በበረት ውስጥ እነሆ ተወለደ!

በመዝሙርና ሥነ ጥበባት ክፍል

ታኅሣሥ ፳፰፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 

      ያቺ ድንግል ቤተ መቅደስ ሆና ሐርና ወርቅ ስታስማማ፣

መልአኩ የምትወልጅው ኢየሱስ ነው ያላትን ቃል ሳታቅማማ፣

የሚፈውስ ድውያንን፣

የሚያበራ ዕውራንን ፣

የሚተረትር ሽባዎችን ፣

የሚያነጻ ለምጻሞችን ፣

 የሚያወጣ አጋንንትን፣

ከስም በላይ ስም የሆነ፣

አልፋ ኦሜጋ የታመነ፣

ድንቅ መካር ሰው መሆንን የወደደ፣

በበረት ውስጥ እነሆ አሁን ተወለደ!

በአርያም የሚኖሩት መላእክቱ፣ ተመልክተው አምላክ ሲያዝን ለፍጥረቱ፣

ግርግም ከበው የዚያ ሕፃን ሠራዊቱ፣

በሰማያት አመስግነው እግዚአብሔርን

በምድር ላይ ለሰውም ልጅ ሰላም ይሁን

ብለው ዘምረው፣ ቤተ ልሔም የምድር ዙፋን፣

በአርያም ተሸክመው ቅዱስ አንተ የሚሉትን፣

ድንግል ማርያም ወዮሴፍ ላም አህያ ተመስለው አርባዕቱን፣

እነርሱ አንቺን ተሸክመው አንቺ ድገሞ ጸባኦትን

የአስተርእዮ ዘመን ሆኖ በምድር ላይ ሲከናወን

የሰማዩ ድንቅ ሥራ፣ ከበረት ውስጥ ሲፈነጥቅ ድህነት ፈውስን

ያነገበ የጽድቅ ጮራን፣

አንቺ ቅድስት ቤተ ልሔም፣

ቅጠል ለብሶ እንደ ሕፃን እያነባ መድኃኔ ዓለም፣

ኃያል ንጉሥ እርቃን ሆኖ ባንቺ ሲድር አልፈራሽም

እንደ ባሕር አልሸሸሽም

እንደ እምቦሳም አልዘለልሽም፡፡

እነ ኪሩብ በነደ እሳት የተሠሩ፣

በሁለት ክንፍ በዓለም ዙሪያ የሚበሩ፣

በመለኮት እሳትነት እንዳይጠፉ በሁለት ክንፍ ፊታቸውን የሠወሩ፣

በቀራቸው በሁለቱ እግራቸውን የጠፈሩ፣

 

  • ቅዱስ (፫)  ብለው ያለፋታ በመንቀጥቀጥ የሚያመልኩት፣

በግርግም ውስጥ እንደ ሕፃን ሲያለቅስ አይተው ምንስ አሉት

ፀሐይና ከዋክብትን ለፈጠረ፣

በልዩ ጌጥ ዓለማትን ላሳመረ፣

ነገሥተ ተርሴስ ወደሴያት፣

እጅ መንሻ አመሃውን ላመጡለት፣

ከዋክብትን በስማቸው ለሚጠራ፣

ፍጥረታትን ያለሳንካ ለሚሠራ፣

ከክብር አንሶ በራፊ ጨርቅ ተጠቅልሎ፣

አምላክ ሳለ ፍጡር መስሎ እንደ ነዳይ ተጎሳቁሎ፣

የዚያ ሌሊት ቢያይል ቁሩ፣

በደመ ነፍስ የሚኖሩ  ትንፋሽ ሰጥተው ሲገብሩ፣

መላእክቱ ቅዱስ(፫) ብለው በፍቅር ሆነው

የሚያመልኩት፣ በግርግም ውስጥ እንደ ሕፃን ሲያለቅስ አይተው

ምንስ አሉት ጽድቃችንም የመርገም ጨርቅ ከንቱ ሆኖ፣

መኖሪያችን በሲኦል ቋት ተወስኖ፣

ለዘመናት ስንገረፍ በእሳት ላንቃ፣

ያበቃ ዘንድ ይህ እንግልት ይህ ሰቆቃ፣

ልዑል ሁይ ክንድህን ስደድ፣

ናማ ውረድ

ና ተወለድ

ብለው ጻድቃን ሲጸልዩ ለዘመናት ፣

እርግማኑን ይሽረው ዘንድ በምርቃት፣

እነሆ አሁን

ጨለማውን አስወግዶ ብርሃኑን ያበራልን፣

ከጎሞራ ያልመሰለን ከሶዶም ግብር ያልደመረን፣

ሰማያትን በደመና የሚጋርድ፣

ተወለደ በዐውድ

እሰይ እሰይ ይኸው አሁን የምሥራች፣

የጸብ ግርዶሽ ተቀዳዶ ሰላም ሆኗል በላ በታች፡፡

፶፻፭፻ የንስሐ የጣር ዘመን ተፈጸመ

አምላክ ወሰብእ በግርግም ውስጥ ከበጎች ጋር ከተመ!

 

 

 

የሃይማኖት ተክል!

ታኅሣሥ ፳፫፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ድንቅ በሆነው የፈጣሪ ሥራ ሰው ሆነን ተፈጥረን በዚህ ዓለም ላይ ስንኖር የሕይወታችን መሠረት በሆነው ሃይማኖት ጸንተንና በቀናው መንገድ ተጉዘን የመንፈስ ፍሬን ለማፍራት እንዲቻለን ነው፡፡ የማንኛውም መንፈሳዊነት መሠረት ሃይማኖት ነውና፡፡ አንድ አምላክን ማመን ለእርሱ መታመን ሃይማኖት ነውና፤ ይህ ምሥጢር ገብቷቸው፣ በድንቅ ሥራቸው አብርተው፣ ፍጹም ተጋድሎአቸውን ጨርሰው ለአምላካቸው እውነተኛ ምስክሮች በመሆን ርስተ መንግሥተ ሰማያትን የወረሱ ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን የቤተ ክርስቲያናችን ዕንቁ ፈርጥ በመሆናቸው እናከብራቸዋለን፡፡

“የሃይማኖት ተክል” የተባለው ቅዱስ አባታችን ኢትዮጵያዊው ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የከበረች ልደት በዓሉ በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ይከበራል፡፡ ጻድቁ በብሥራተ ቅዱስ ሚካኤል መሠረትም በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ልዩ ስሙ ኢቲሳ በሚባል ቦታ መጋቢት ፳፬ ተፀንሰው ታኅሣሥ ፳፬ የተወለዱት ከአባታቸው ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው እግዚ ኅረያ ነው፡፡

በተለወዱ በሦስተኛው ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ     ወርደው    ‹‹ሐዱ  አብ  ቅዱስ፤   አሐዱ  ወልድ  ቅዱስ፤  አሐዱ  ውእቱ  መንፈስ  ቅዱስ፤  አንዱ  አብ  ቅዱስ  ነው፤  አንዱ  ወልድ  ቅዱስ  ነው፤  አንዱ  መንፈስ  ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት አጋእዝተ ዓለም ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ ወላጆቻቸው ያወጡላቸው ስም ‹‹ፍሥሐ ጽዮን››  የሚል ቢሆንም‹‹ተክለሃይማኖት›› ደግሞ ጌታችን እራሱ ነው፡፡

የሃይማኖት ተክል የተባሉት ቅዱስ አባታችን የወንጌልን ቀንበርን ተሸክመው፣ ሀገራችን ኢትየጵያን በዕርፈ መስቀል ያረሱ፣ ቅዱስ ቃሉን ሰብከውና አስተምረው፣ እውነተኛ ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ሃይማኖትን ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን ለዓለም አሳውቀው፣ ጣዖታትን ሰባብረው ቀጥቅጠው ያጠፉ፣ ብዙዎችን ከኃጢአት ጎዳና መልሰው ለርስተ መንግሥተ ሰማያት ያበቁ ታላቅ አባት ናቸው፡፡

የአባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ጸሎት፣ አማላጅነትና ረድኤት አይለየን፤ አሜን!!!

ምንጭ፡ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት

 

‹‹እነርሱ በእምነት የእሳት ኀይልን አጠፉ›› (ዕብራውያን ፲፩፥፩)

ታኅሣሥ ፲፯፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ለብዙዎቻችን እሳትን የሚያጠፋው ውኃ ብቻ ይመስለናል፡፡ ለእግዚአብሔር የታመኑ ቅዱሳን ሰማዕታት የእሳትን ኃይል በትዕግሥታቸው እንዳጠፉትና ጸሎታቸውም ለእኛ በአማላጅነታቸው ለምንታመን ምእመናን ሁልጊዜም እንደሚያስፈልገን ፈልፈለ ማኅሌት የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ምስክር ሆኖ ያስተምረናል፤ አጥፍኡ ኃይለ እሳት በትዕግሥቶሙ፤ ይብጽሐነ ወትረ ጸሎቶሙ፤በትዕግሥታቸው የእሳትን ኃይል አጠፉ፤ ጸሎታቸው ዘወትር ይድረሰን” እንዲል፤ (ድጓ ዘታኅሣሥ ፪)

በሐዲስ ኪዳን ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እምነት ማለት ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የምታረጋግጥ ፣ የማናየውንም ነገር የምታስረዳ ናት››  በማለት የተናገረውን ቃል (ዕብራውያን ፲፩፥፩) በብሉይ ኪዳን አስቀድሞ በተፈፀመ ገድል እንድናውቀው የሠለስቱ ደቂቅ የባቢሎን የዱራ ሜዳ ገድልና የእምነት ጽናት ዓይነተኛ የሕይወት ትምህርት እንዲሆነን በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎልን እናገኛዋለን፡፡ እምነታችን እውነተኛ ሆኖ የሚገለጠው እግዚአብሔር በሚፈጽምልን የትድግና ሥራ ብቻ ሳይሆን መከራም ቢመጣ የመጣው እግዚአብሔር ፈቅዶ በመከራው ተፈትነን ካለፍን በኋላ እኛ ልጆቹ እንድናገኝ የፈለገውን ሰማያዊ አክሊልና ዋጋ እንድናገኝም ስለሚፈልግ መሆኑን ማመን ስንችል ነው፡፡

ጻድቁ አባታችን ቅዱስ ኢዮብ  እጅግ ብዙ መከራ ሲደርስበት ‹‹ከእግዚአብሔር እጅ መልካሙን ተቀበልን፤ ክፉውን ነገርስ አንታገሥምን?›› በማለት በደረሰበት ነገር ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት በከንፈሩ ሳይበድል የሕይወቱን የፈተና ጊዜ ለማሳለፍ በቅቷል፡፡ (መጽሐፈ ኢዮብ ፪፥፲) የሠለስቱ ደቂቅ እውነተኛ እምነትም ለናቡከደነፆር በሰጡት ምላሽ ውስጥ የምናገኘው ነው፡፡ ንጉሥ ናቡከደነፆርም እኔ ላሠራሁት ምስል ስገዱ ባላቸው ጊዜ  ‹‹ናቡከደነፆር ሆይ! በዚህ ነገር እንመልስልህ ዘንድ አንፈልግም፡፡ ንጉሥ ሆይ! እኛ የምናመልከው አምላክ በሰማይ አለ፤  ከሚነድደው ከእሳቱ እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል፤ ንጉሥ ሆይ! ይህም ባይሆን ፣ አማልክትህን እንዳናመልክ ፣ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንዳንሰግድለት ዕወቅ›› አሉት፡፡ (ትንቢተ ዳንኤል ፫፥፲፭-፲፰)

ከዚህ በኋላ ወደ እሳት እንዲጨመሩ ንጉሡ አዘዘ፡፡ አይደለም እሳት ላይ ተጥደን በመልካም ሁኔታ ውስጥ ሆነን እንኳን የእግዚአብሔርን ስም መጥራት ላቃተን ለእኛ፣ ሠለስቱ ደቂቅ በእሳት መካከል ሆነው የእግዚአብሔርን ስም መጥራት ብቻ ሳይሆን ረጅም ጸሎትን ሲያደርሱ

 

እንደነበር ማወቅ ምንኛ ግሩም ነው! (ወጸለዩ ማዕከለ እቶነ እሳት ነዋኃ ጸሎተ) (መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ታኅሣሥ ፪)፡፡

በመከራ ላይ መከራ ቢያጸኑባቸው በምስጋና ላይ ምስጋና በመጨመር ታላቅ የሆነ የነገረ ክርስቶስ ትምህርትንም የያዘ ጸሎት ያደረሱት በእሳት ውስጥ ነው ቢባል ማን ያምናል፡፡ በጸሎታቸው እነርሱ ይህን ገድል ከፈፀሙ ከ፮፻ ዓመት በኋላ አምላክ የሰውን ሥጋ ለብሶ ተገልጦ እንደሚወለድ እና በዚህች ምድርም ፴፫ ዓመት እንደሚቆይ የሚያጠይቅ ነው፡፡

ሰው እግዚአብሔርን ካመነና ማመኑንም በሥራ ገልጦ ካከናወነ ፍጹም የሆነ የእግዚአብሔር ረድኤት ከእርሱ ጋር ስለሚሆን በሥጋ ዓይን ስናየው በሥጋው ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርስበት የሚችል እሳት እንኳን አቅም ያጣል፡፡ ሠለስቱ ደቂቅን ወደ እሳት ወርውረው እንዲጨምሩ በንጉሡ የታዘዙትን ሰዎች የገደለ እሳት በመካከሉ የተገኙ ሠለስቱ ደቂቅ ላይ ግን አንዳች ጉዳት ማድረስ አልቻለም፡፡ የራሳቸው ጠጉር አንዲት ዘላላ እንኳ አልተቃጠለችም፤  ሰናፊላቸውም አልተለወጠም፤ ሽታቸውንም አልለወጠም፡፡ (ትንቢተ ዳንኤል ፫፥፳፯)

ጥንተ ጠላት ዲያቢሎስ በዓላውያን ነገሥታት ላይ አድሮ ዛሬም በእኛ ላይ የጥላቻን እሳት እያነደደ ከራሳችን አልፎ ለሀገራችን ኢትዮጵያም የሚተርፍ መከራን አኑሯል፡፡ የባቢሎንን እሳት በመስቀሉ በማቀዝቀዝ ሠለስቱ ደቂቅን ከእግዚአብሔር ተልኮ ያዳነው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በእኛና በሀገራችን ኢትዮጵያ እየነደደ እጅግ መከራ ውስጥ የከተተንን የጥላቻ እሳት እንዲያበርድልንና ሁላችንም የፍቅር ሰው እንድንሆን አማላጅነቱና ጠብቆቱ አይለየን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

 

በአታ ለእግዝእትነ ውስተ ቤተ መቅደስ

ከደጋጎቹ ቅዱሳን አባቷና እናቷ ኢያቄምና ሐና የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ቀን የከበረ ነው፡፡ በበጎ ምክር በእግዚአብሐርም ፈቃድ ይህ ሆነ፤ በዚያን ጊዜ ኢያቄምና ሐና “….ሆዷ ዘመድ ሳይወድ አፏ እህል ሳይለምድ ወስደን እንስጥ” ብለው በመማከር መባዕም ጨምረው ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ፡፡   

ተዝካረ ልደቱ ለኤልያስ ነቢይ

ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ቅዱሳት መጻሕፍት ነቢዩ ኤልያስ የተወለደው በታኅሣሥ ፩ ቀን ከነገደ ሌዊ እንደሆነ ይገልጻሉ፤ የአባቱ ስም ኢያስንዩ የእናቱ ስም ቶና ይባላሉ፡፡ በተቀደሰች የልደት ቀኑም አባቱ ብርሃን የለበሱ አራት ሰዎች ሲሰግዱለትና ሕፃናት በሚጠቀልሉበት ጨርቅ ፈንታ በእሳት ሲጠቅልሉት  ተመልክቷል፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ዘኅዳር ፩፣ መዝገበ ታሪክ ገጽ ፹፬)

ኢትዮጵያ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተአምኆ ቅዱሳን መጽሐፉ ስለዚሁ ነቢይ እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ “ቴስቢያዊ (የቴስቢያ ሰው)፤ ኮሬባዊ (ወደ ኮሬብ ተራራ የወጣ)፣ ታቦራዊ (በታቦር ተራራ የተገኘ)፣ ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን የለጐመ ለሆነ፣ የጸሎቱ ቃልም በአዶናይ ዦሮ ውስጥ ለተሰማ፣ ውኃውን እስኪበላ ደርሶ እሳትን ከሰማይ ያወረደ ለሆነ፣ በእሳት ሠረገላ ተጭኖ ወደ ተድላ ደስታ ቦታ ለገባ ለነቢዩ ለኤልያስ ሰላምታ ይገባል።”

ሊቁ አርከ ሥሉስም በአርኬ መጽሐፉ ላይ ደግሞ እንዲህ ብሏል፤ “ምድራዊ የሆነ የዓለም ሕይወትን አራግፈህ ለማረፍ ወደ ሰማያት ያረግህ ለሆንክ ለአንተ ለኤልያስ ሰላም እላለሁ፡፡ አክአብን ለተናቀ ሥራው እየዘለፍከው ጣዖታትን የቀጠቀጥክ ማምለኪያዎቹን ያፈረስክ በምስጋናህ ምንኛ ተመሰገንህ።”

ቅዱሱ መጽሐፍ የዚህን ፈፍ  ነቢይ ስም “ኤልያስ” ፻ (መቶ) ጊዜ ጠቅሶታል፡፡ ድንቃ ድንቅ ተአምራቱንም መዝቦት እናገኛለን፤ ከእነዚህም መካከል አክአብና ኤልዛቤል ጣዖት በማምለከታቸው ኤልያስ ሦስት ዓመት ከ ስድስት ወር ዝናብን በጸሎቱ አቁሟል፡፡ (፩ኛ ነገ. ፲፯)፤ የሰራጵታዋን መበለት የሞተ ልጇን አስነሥቷል፡፡ (፩ኛ ነገ.፲፯፥፲፱)

ለአምላካችን እግዚአብሔር ያቀረበውን መሥዋዕት እሳት ከሰማይ ወርዶ የበላለት ነቢይ እንደሆነም መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፤ (፩ኛ ነገ ፲፰) ከሦስት ዓመት ከስድስት ወር በኋላ ቀርሜሎስ ወጥቶ በመጸለይ ዝናብ እንዲዘንብ አድርጓል፤ (፩ኛ ነገ. ፲፰) አካዝያስ የላካቸውን ፶ (ኀምሳ) አለቃዎች እሳት ከሰማይ አውርዶ አቃጥሏል፤ (፪ኛ ነገ. ፩) በመጐናጸፊያው የዮርዳኖስን ወንዝ ከፍሏል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፬) በእሳት ሠረገላ በዐውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጥቷል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፩)፣ በደብረ ታቦር ጌታ ምሥጢረ መንግሥቱን ሲገልጽ ከሙሴ ጋር ዐብሮ ተገኝቷል፤ (ማቴ.፲፯፥፬) ዳግመኛ በመምጣት በሐሳዌ መሲሕ ጊዜ ሰማዕትነትን ይቀበላል፡፡ (ማቴ.፲፯፥፲፩)

የነቢዩ ኤልያስ በረከት ይደርብን!

 

አጠንተ መንበሩ!

ኀዳር ፳፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

አልፋና ኦሜጋ የሆነው አምላካችን ቅድመ ዓለም አስቀድሞ ሲለሠስ ሲቀደስ እንደኖረ ሁሉ ድኅረ ዓለም በፍጥረታቱ ሁሉ ሲመሰገን፣ ሲቀደስና ሲከበር ይኖራል፡፡ ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ የፈጠራቸው መላእክትና ሰውም ይህን ግብር የሚሠሩ ቀደምት ፍጥረታት ናቸው፡፡ (መጽሐፈ አክሲማሮስ ዘእሑድ)

የአምላካችን እግዚአብሔር ምስጋና በሰማይና በምድር ነው፤ በዓለመ መላእክት ዘወትር “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ” እያሉ ከሚያመሰግኑት መላእክት ሁሉ በላይ “አጠንተ መንበሩ” ተብለው የሚጠሩት “ካህናተ ሰማይ” ናቸው፡፡ በምድር ባለች ማኅደረ መለኮት የአምላክ ማደሪያ ቤተ ክርስቲያን ምድራዊ ካህናት በታቦቱ ፊት ማእጠንት እያጠኑ እንደሚያመሰግኑ ሁሉ፣ ቅዱሳን ሱራፌል ሃያ አራቱ ካህናትም የቅድስት ሥላሴን መንበር እያጠኑ ሳያቋርጡ ያመሰግናሉ፡፡

ነቢዩ ኢሳይያስም ስለ እነርሱ ሲናገር እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ንጉሥ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን በረዥምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀምጦ አየሁት፤ የልብሱም ዘርፍ መቅደሱን ሞልቶት ነበር። ሱራፌልም ከርሱ በላይ ቆመው ነበር፥ ለእያንዳንዱም ስድስት ክንፍ ነበረው፤ በሁለት ክንፍ ፊቱን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ እግሮቹን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ ይበር ነበር። አንዱም ለአንዱ፦ ‘ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፣ ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች’ እያለ ይጮኽ ነበር።›› (ኢሳ.፮፥፩-፭) ቅዱስ ዮሐንስ ደግሞ ‹‹በዙፋኑ ዙሪያም ሃያ አራት ዙፋኖች ነበሩ፥ በዙፋኖቹም ላይ ነጭ ልብስ ለብሰው በራሳቸውም የወርቅ አክሊል ደፍተው ሃያ አራት ሽማግሌዎች ተቀምጠው ነበር›› ብሏል፡፡ (ራእይ ፬፥፬)

እነዚህ ቅዱሳን መላእክት ሱራፌል ሥጋ የሌላቸው ረቂቅ የእውነት ካህናት ናቸው፡፡ ከሰማያዊ ሠራዊት ሁሉ ከፍ ከፍም ይላሉ፡፡ የሰው ልጆችን ጸሎት፣ ምጽዋትንና ጽድቅን በልዑል እግዚአብሔር ፊት ያቀርባሉ፡፡ የሚጸለየውን ጸሎትና የሚሠዋውን መሥዋዕት በማዕጠንታቸው እያሳርጉ ሕያዋን ሆነው ይኖራሉ፤ አይሞቱም፤ አይለወጡም፡፡

በከበረች ኅዳር ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን የስማቸው ትርጓሜ ሱራፌል “አጠንተ መንበሩ ለልዑል፣ ኤልሻዳይ” የሆነ ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው፤ አባታችን ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑበት ዕለት  ነው፡፡

የቅዱሳን መላአክት ሱራፌል፣ የቅዱሱ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ይደርብን!

ጽዮን ማርያም

ኀዳር ፲፱፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 ጽዮን “”ጸወን” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን “አምባ፣ መጠጊያ” ማለት ነው፡፡ እመ ብዙኀን የሆነችውን የአምላክ እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚገለጽ መሆኑን  “ማኅደረ አምላክ” በሚለው ትርጒም እንረዳለን፡፡ ጽዮን የሚለው ስያሜ በቁሙ ለታቦት፣ ለጽላት ሲያገለግል በትንቢታዊ ምሥጢሩ ግን ለድንግል ማርያም፣ ለቤተ ክርስቲያንና ለዘለዓለማዊት ርስተ መንግሥተ ሰማያት ያገለግላል::

ታቦተ ጽዮን “ጽላተ ኪዳን፣ ታቦተ ሕጉ” እየተባለችም ትጠራለች:: “ጽሌ” ማለት “ሰሌዳ” ማለት ሲሆን “ጽላት” ደግሞ በብዙ ቁጥር ነው:: “ኪዳን” ደግሞ በፈጣሪና በሰው ልጆች መካከል ያለ “ውል፣ ስምምነት” ነው፡፡ ታቦተ ጽዮን ዐሥርቱ ቃላት የተጻፈባት በመሆኗ የእግዚአብሔር ሕግጋትን የያዘ ናት፡፡ በዚህም በሕጉ እንድመራ ትእዛዙን እንድፈጽም ያሳስበናል፡፡

አልፋና ኦሜጋ፣ ኤልሻዳይ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር አስቀድሞ ለእስራኤል ሕዝብ ቅድስት የምትሆን ማደሪያውን ታቦተ ጽዮንን በነቢዩ ሙሴ አካማኝነት የሰጣቸው ክብር፣ ሞገስ፣ አምባ እንድትሆናቸው ነው፡፡ (ዘጸ. ፴፩፥፲፰)  ለ፭፻ (አምስት መቶ) ዓመት ከእነርሱ ሳትለይ ከአምላክ ጋር መገናኛ፣ በጦርነት ጊዜም ማሸነፊያ ኃይላቸው ሆናም ኖራለች፡፡

ሀገረ እግዚአብሔር የሆነችው ኢትዮጵያም ለከበረች ታቦተ ጽዮን መቀመጫ ለመሆን ታድላለች፡፡ በቀዳማዊው እብነ መለክ፣ እብነ ሐኪም/በቀዳማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት አማካኝነት ወደ ሀገራችን የመጣችው ታቦቷ እስከ አሁን ድረስ በአክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን እንደምትገኝ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይናገራሉ፡፡ (መጽሐፈ ክብረ ነገሥት) የጌታችን ድንቅ ቸርነት የተደረገልን እኛ የድንግል ማርያም የዐሥራት ልጆች የአምላክን ሥራ ልናደንቅና ልናመሰግን ይገባል፡፡

ሀገራችን የገባበትን እንዲሁም አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን የተቀመጠበት ኅዳር ፳፩ ቀንንም ታላቅ በዓልን እናደርጋለን፡፡

የአምላካችን እግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፤ አሜን!

 

“ይትሌዓል መንበሩ!” ቅዱስ ያሬድ

ኀዳር ፲፩፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

አሸናፊና ኃያል፣ ሁሉን ቻይ የሆነ የእግዚአብሔርን ገናንነትና እርሱን የሚመስል አምላክ እንደሌለ የሚያመለክት የስሙ ትርጓሜ “መኑ ከመ አምላክ፤ እንደ አምላክ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?” የሆነ፣ የመላእክት ሁሉ አለቃ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በኅዳር ፲፪ የተሸሞበት ቀን “እግዚኡ ረሰዮ ለውእቱ ሚካኤል እምኵሎሙ መላእክት ይትሌዓል መንበሩ፤ ጌታው ሚካኤልን ከመላእክት ሁሉ መንበሩን ከፍ ከፍ አደረገው” እየተባለ ይከበራል፡፡

የእግዚአብሔር ሠራዊት ሁሉ አለቃ የሆነው መልእኩ ሚካኤል መላእክትን ሁሉ የሚያዝ ነው፡፡ መላእክት ደግሞ አለቃቸውን ያከብራሉ፤ ይታዘዛሉ፤ ከትእዛዙም አይወጡም፡፡ ሳጥናኤል በትዕቢቱ ከክብሩ ተዋርዶ ወደ ምድር ሲጣል አምላክ ቅዱስ ሚካኤልን በእርሱ ፈንታ በዐሥሩ ከተማ በመቶውም ነገደ መላእክት ላይ ሾሞታል፡፡ የእግዚአብሔር ሕዝብ በሆኑት ላይ ጭምርም ሾመው፡፡ … ዐይኑን አንሥቶ ተመለከተ፤ እነሆም የተመዘዘ ሰይፍ የያዘ ሰው በፊቱ ቆመ፤ ኢያሱም ወደ እርሱ ቀርቦ፤ “ከእኛ ወገን ወይስ ከጠላቶቻችን ወገን ነህ? አለው፡፡ እርሱም “እኔ የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ሆኜ አሁንም ወደ አንተ መጥቼአለሁ”  እንዲል፡፡ (ኢያ.፭፥፲፫)

ሠራዊተ መላእክት የሚያከብሩትንና የሚታዘዙለትን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን እኛም እንደ ነቢዩ ኢያሱ እናከብረዋለን፤ እንታዘዘዋለን፡፡ መላእክትን ማክበርና መታዘዝ እንደሚገባ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡፡ “በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀሁትም ሥፍራ ያገባህ ዘንድ እነሆ እኔ መልአክህን በፊትህ እሰዳለሁ፤ በፊቱ ተጠንቀቁ፤ ቃሉንም አድምጡ፤ ስሜም በእርሱ ስለሆነ ኃጢአት ብትሠሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት፤ አንተ ግን ቃሉን ብትሰማ፣ ያልሁህንም ሁሉ ብታደርግ፣ ጠላቶችህን እጣላቸዋለሁ፣ የሚያስጨንቁህንም አስጨንቃቸዋለሁ፣ መልአኬ በፊትህ ይሄዳልና…፡፡” (ዘጸ.፳፫፥፳-፳፪)

በበዓሉ መታሰቢያ በኅዳር ፲፪ ቀን የክብር ባለቤት በሆነ በእግዚአብሔር ፈቃድ ክንፎቹን ወደ ሲኦል ያወርዳል፤ ኃጥአንንም ወደ አዲሲቱ ምድር ያወጣቸዋል፤ ይኸውም የመላእክት አለቃ የሚካኤል ሠራዊት ይሆናሉ፡፡ ይቅርታ የተደረገላቸውና ምሕረት አግኝተው በአንድ ጊዜ በክንፉ ያወጣቸው ስፍር ቁጥር የላቸውም፡፡ ቅዱስ ሚካኤል በየዓመቱ በኅዳር ፲፪ ቀን እንዲህ እያደረገ እልፍ ነፍሳትን ያወጣል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ወገኖች የሆኑትን ሁሉ እንደ ሥራቸው ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ይወስዳቸዋል፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ አብ መጋረጃ ውስጥ ይገባል፤ በዚህች ዕለት ምድራዊትና ሰማያዊት ስለሆነች ምሕረቱም ከመንበሩ በታች ይሰግዳል፡፡ ስለውኃ ምንጮች፣ ስለ ወይን ቦታዎች፣ ስለ ምድር ፍሬዎች በምድርም ላይ ስለሚኖሩ ስለ ሰው ልጆች ነፍስ ሁሉ፣ ስለ እንስሳትም፣ ስለ ሰማይ ወፎችም፣ ስለ ባሕር ዓሣዎችም፣ በምድር ላይና በባሕር ውስጥ ስለሚንቀሳቀሱ ሁሉ የምሕረት ባለቤት ከሆነ ከአብ ዙፋን በታች ሁልጊዜ በማመስገን ይሰግዳል፤ ልመናውንም እስኪሰማውና የምሕረትንም ቃል እስኪያስተላልፍለት ድረስ ከእግረ መንበሩ ሥር አይነሣም፡፡

ለዚህ ዓለም ምሕረትን የሚለምኑ ቅዱሳን መላእክትም በየዓመቱ ኅዳር ፲፪ ቀን በእግዚአብሔር የዙፋኑ ዐውደ ምሕረት ዙሪያ ተሰብስበው ስለ ሰውና ስለ እንስሳትም ሁሉ ምሕረትን የሚለምን ቅዱስ ሚካኤል ከአብ መጋረጃ ውስጥ በወጣ ጊዜ ቸርና መሐሪ አብ ለቅዱስ ሚካኤል የሰጠው ልብሱን እነዚያ መላእክት ይመለከታሉ፤ ይቅርታን የማግኘት ምልክታቸው ነውና፡፡ ስለዚህ እነዚህ ቅዱሳን መላእክት በምድር ላይ ምሕረት እንደተደረገ ሰውንም እንስሳትንም ይቅር እንዳለ በዚህ ዓለምም የሚሆነውን ሁሉ አይተው ቅዱስ ሚካኤል በለበሰው ልብስ አምሳል ያውቁታል፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር እንደሚለው ይህ እጅግ የከበረ ገናና መልአክ ቅዱስ ሚካኤል “ከቅዱሳን ሰማዕታት ጋራ በመሆን ገድላቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ የሚያጽናናቸውና የዘወትር ጠባቂአቸው ሆኖ የሚራዳቸው እርሱ ነው፡፡” የብዙዎቹንም ቅዱሳን ገድል ስንመለከት የዘወትር ጠባቂያቸው ቅዱስ ሚካኤል ነው፡

መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ያደረገውም ተአምር ይህ ነው፡- የእግዚአብሔር ወዳጅ የሆነ ስሙ ዱራታዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፡፡ የሚስቱም ስም ቴዎብስታ ነው፡፡ እነርሱም ሁልጊዜ ያለማቋረጥ የዚህን የከበረ መልአክ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ያደርጉ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ በሀገር ውስጥ ችግር በሆነ ጊዜ ገንዘባቸው አለቀ፡፡ ለቅዱስ ሚካኤልም ለበዓሉ መታሰቢያ የሚያደርጉትን እስኪያጡ ድረስ ቸገራቸው፡፡ ዱራታዎስም ሸጦ ለመልአኩ በዓል መታሰቢያ ያደርገው ዘንድ የእርሱንና የሚስቱን ልብስ ይዞ ወጥቶ ሄደ፡፡

የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም በታላቅ መኰንን አምሳል ለዱራታዎስ ተገልጦ ወደ ባለጸጎች ሄዶ በእርሱ ዋስትና በአንድ ዲናር አንድ በግ እንዲወስድ፣ ሁለተኛም ወደ ባለ ስንዴ ዘንድ ሄዶ በእርሱ ዋስትና ስንዴን እንዲወስድ ዳግመኛም ወደ ዓሣ አጥማጅ ዘንድ ሄዶ አንድ ዓሣ እንዲወስድ ነገር ግን ወደ ቤቱ ሳይርስ የዓሣውን ሆድ እንዳይቀድ አዘዘው፡፡ ዱራታዎስም እንደታዘዘው አደረገ፡፡ ቤቱም በተመለሰ ጊዜ ቤቱ ሁሉ በበረከት ተመልቶ አገኘው፡፡ እርሱም እጅግ ተደስቶ የዚህን የክበር መልአክ የመታሰቢያውን በዓል አደረገ፡፡ ጦም አዳሪዎችንና ድኆችን ጠርቶ አጠገባቸው፡፡

ከዚህም በኋላ ለዱራታዎስና ለሚስቱ ቅዱስ ሚካኤል ሁለተኛ ተገለጠላቸው፡፡ ዱራታዎስንም የዓሣውን ሆድ እንድሰነጥቅ አዘው፡፡ በሰነጠቀውም ጊዜ ፫፻ (ሦስት መቶ) የወርቅ ዲናር በዓሣው ሆድ ውስጥ ተገኘ፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ዱራታዎስንና ሚስቱን ቴዎብስታን እንዲህ አላቸው፤ “ከዚህ ዲናር ወስዳችሁ ለባለ በጉ፣ ለባለ ዓሣውና ለባለ ስንዴው ዕዳችሁን ክፈሉ፡፡ የቀረውም ለፍላጎታችሁ ይሁናችሁ፤ እግዚአብሔር አስቧችኋልና በጎ ሥራችሁን፣ መሥዋዕታችሁንና ምጽዋታችሁን አስቦ በዚህ ዓለም አሳመረላችሁ፤ በኋለኛውም መንግሥተ ሰማያትን አጀጋጀላችሁ” አላቸው፡፡

እነርሱም ይህን ነገር ሲሰሙ ደነገጡ፡፡ የከበረ ገናናው መልአክም “ከመከራችሁ ሁሉ ያዳንኳችሁ የመላእክት አለቃ እኔ ሚካኤል ነኝ፤ መሥዋዕታችሁንና ምጽዋታችሁን ወደ እግዚአብሔር ፊት ያሳረግሁ እኔ ነኝ፡፡ አሁንም በዚህ ዓለም ከበጎ ነገር እንድታጡ አላደርጋችሁም” አላቸው፡፡ ይህንንም ከነገራቸው በኋላ ወደ ሰማያት ወጣ፡፡ እነርሱም በፍርሃትና በክብር ሰገዱለት፡፡

የመላእክት ሁሉ አለቃ የቅዱስ ሚካኤል ጥበቃው፣ ጸሎቱ፣ አማላጅነቱና ተራዳኢነቱ አይለየን፤ ከበዓሉ ረድኤት በረከት ይክፈለን፤ አሜን!

(ምንጭ፡ድርሳነ ቅዱስ ሚካኤል፣ መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ኅዳር)

 

አዘክሪ ድንግል አዘክሪ!

ኀዳር ፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

አዘክሪ ድንግል አዘክሪ
ለልጅሽ አሳስቢ አዘክሪ

ለኃጥአን ለምኝልን
አይደለም ለጻድቃን

ከጠላት ሸሽተሽ ለተሰደድሽበት
በግብጽ በረኀ በሙቀቱ ውዕያት
በዱር በገደሉ በቁር ግሽበት

በጀርባዎችሽ አዝለሽ ለተጓዝሽበት
በመታቸው ተረከዞች እንቅፋት
ያን ሁሉ መከራ ለተቀበልሽበት

ለማዳን ሰውን ከጽኑ ግርፋት
ከሲኦል ትላትል ቁንጥጫ ከገሃነመ እሳት
ለአዳም ዘር በሙሉ የነፍስ ድኅነት
ለምኝልን እናት አትተይን በእውነት

አዘክሪ ድንግል አዘክሪ
ለልጅሽ አሳስቢ አዘክሪ!

የማይሞተው ሞተ!

በመዝሙርና ሥነ ጥበባት ክፍል

ጥቅምት ፳፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ልዑል ሆይ ክንድህን ስደድ

ናማ ውረድ

ና ተወለድ

ብለው ነቢያት በጾም ጸሎት ተጉ ጮኹ!

ጨለማውን አስወግዶ ብርሃኑን ያበራልን

አንጠፋ ዘንድ በፍጹም ፍቅር የራራልን

 

በግብዞች በአይሁድ ሥርዓት

በሕጋቸው እንደጻፉት

የሾህ አክሊል ተቀዳጅቶ

መጻጻውን ተጎንጭቶ

 …..

እርሱ ሞተ ሊሰጥ ሕይወት

ወየው በሉ አልቅሱለት፤

የእጁን መዳን ያገኛችሁ የጌንሴሬጥ ድውይ ሁሉ

ለኢየሱስ አልቅሱለት፤ ፍዳን ስላያት በመስቀሉ

የ፲፪ ዘመን ሥቃይ በልብሱ ጫፍ ………

በቅጽበት ውስጥ የጠፋልሽ

ተገረፈ፤ ተንገላታ፤ የማይሞተው ሞትን ሞተ፤ ……..

ያ ርኅሩኅ ቸር መዳኒትሽ

ኢያሮስ የት ነው ያለህ!

ያ’ዓለም ጌታ ተተፋበት ሴት ልጅህን ያዳነልህ!

እመቤቴ የልጅሽን መከራውን እንዴት ቻልሽው አልልሽም

ቅዱስ ዳዊት በእሳት ፈረስ ሰባቱ ኃያል …..

መላእክቱ ካንቺ መጥተው ቢያፅናኑሽም

ለሦስት ቀን የአንዱ ልጅሽ ከሞቱ ይልቅ አሟሟቱ ….

እያስነባሽ እህል ውኃ እንኳን አልቀመስሽም

አብ ሆይ ማረን!

መንፈስ ቅዱስ ተዘከረን!

በልጅህ ደም የተገዛን ለመሆኑ አላወቅንም ዋጋችንን

ጽድቃችንም የመርገም ጨርቅ ከንቱ ሆኖ

መኖሪያችን በሲኦል ቋት ተወስኖ

ለዘመናት ስንገረፍ በእሳት ላንቃ

ያበቃ ዘንድ ይህ እንግልት ይህ ሰቆቃ

እሰይ እሰይ ይኸው አሁን የምሥራች

የሞት ዐዋጅ ተሻረልን፤ ገነት ዳግም ተከፈተች

የጥሉ ግድግዳ ፍርሶ ሰላም ሆኗል ከላይም ከታች

፶፻፭፻ የንስሐ የጣር ዘመን ተፈፀመ

በደላችን ተሰርዞ በክርስቶስ ደም ታተመ::