በአታ ለእግዝእትነ ውስተ ቤተ መቅደስ
ከደጋጎቹ ቅዱሳን አባቷና እናቷ ኢያቄምና ሐና የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ቀን የከበረ ነው፡፡ በበጎ ምክር በእግዚአብሐርም ፈቃድ ይህ ሆነ፤ በዚያን ጊዜ ኢያቄምና ሐና “….ሆዷ ዘመድ ሳይወድ አፏ እህል ሳይለምድ ወስደን እንስጥ” ብለው በመማከር መባዕም ጨምረው ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ፡፡
ከደጋጎቹ ቅዱሳን አባቷና እናቷ ኢያቄምና ሐና የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ቀን የከበረ ነው፡፡ በበጎ ምክር በእግዚአብሐርም ፈቃድ ይህ ሆነ፤ በዚያን ጊዜ ኢያቄምና ሐና “….ሆዷ ዘመድ ሳይወድ አፏ እህል ሳይለምድ ወስደን እንስጥ” ብለው በመማከር መባዕም ጨምረው ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ፡፡
ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
ቅዱሳት መጻሕፍት ነቢዩ ኤልያስ የተወለደው በታኅሣሥ ፩ ቀን ከነገደ ሌዊ እንደሆነ ይገልጻሉ፤ የአባቱ ስም ኢያስንዩ የእናቱ ስም ቶና ይባላሉ፡፡ በተቀደሰች የልደት ቀኑም አባቱ ብርሃን የለበሱ አራት ሰዎች ሲሰግዱለትና ሕፃናት በሚጠቀልሉበት ጨርቅ ፈንታ በእሳት ሲጠቅልሉት ተመልክቷል፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ዘኅዳር ፩፣ መዝገበ ታሪክ ገጽ ፹፬)
ኢትዮጵያ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተአምኆ ቅዱሳን መጽሐፉ ስለዚሁ ነቢይ እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ “ቴስቢያዊ (የቴስቢያ ሰው)፤ ኮሬባዊ (ወደ ኮሬብ ተራራ የወጣ)፣ ታቦራዊ (በታቦር ተራራ የተገኘ)፣ ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን የለጐመ ለሆነ፣ የጸሎቱ ቃልም በአዶናይ ዦሮ ውስጥ ለተሰማ፣ ውኃውን እስኪበላ ደርሶ እሳትን ከሰማይ ያወረደ ለሆነ፣ በእሳት ሠረገላ ተጭኖ ወደ ተድላ ደስታ ቦታ ለገባ ለነቢዩ ለኤልያስ ሰላምታ ይገባል።”
ሊቁ አርከ ሥሉስም በአርኬ መጽሐፉ ላይ ደግሞ እንዲህ ብሏል፤ “ምድራዊ የሆነ የዓለም ሕይወትን አራግፈህ ለማረፍ ወደ ሰማያት ያረግህ ለሆንክ ለአንተ ለኤልያስ ሰላም እላለሁ፡፡ አክአብን ለተናቀ ሥራው እየዘለፍከው ጣዖታትን የቀጠቀጥክ ማምለኪያዎቹን ያፈረስክ በምስጋናህ ምንኛ ተመሰገንህ።”
ቅዱሱ መጽሐፍ የዚህን ፈፍ ነቢይ ስም “ኤልያስ” ፻ (መቶ) ጊዜ ጠቅሶታል፡፡ ድንቃ ድንቅ ተአምራቱንም መዝቦት እናገኛለን፤ ከእነዚህም መካከል አክአብና ኤልዛቤል ጣዖት በማምለከታቸው ኤልያስ ሦስት ዓመት ከ ስድስት ወር ዝናብን በጸሎቱ አቁሟል፡፡ (፩ኛ ነገ. ፲፯)፤ የሰራጵታዋን መበለት የሞተ ልጇን አስነሥቷል፡፡ (፩ኛ ነገ.፲፯፥፲፱)
ለአምላካችን እግዚአብሔር ያቀረበውን መሥዋዕት እሳት ከሰማይ ወርዶ የበላለት ነቢይ እንደሆነም መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፤ (፩ኛ ነገ ፲፰) ከሦስት ዓመት ከስድስት ወር በኋላ ቀርሜሎስ ወጥቶ በመጸለይ ዝናብ እንዲዘንብ አድርጓል፤ (፩ኛ ነገ. ፲፰) አካዝያስ የላካቸውን ፶ (ኀምሳ) አለቃዎች እሳት ከሰማይ አውርዶ አቃጥሏል፤ (፪ኛ ነገ. ፩) በመጐናጸፊያው የዮርዳኖስን ወንዝ ከፍሏል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፬) በእሳት ሠረገላ በዐውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጥቷል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፩)፣ በደብረ ታቦር ጌታ ምሥጢረ መንግሥቱን ሲገልጽ ከሙሴ ጋር ዐብሮ ተገኝቷል፤ (ማቴ.፲፯፥፬) ዳግመኛ በመምጣት በሐሳዌ መሲሕ ጊዜ ሰማዕትነትን ይቀበላል፡፡ (ማቴ.፲፯፥፲፩)
የነቢዩ ኤልያስ በረከት ይደርብን!
ኀዳር ፳፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
አልፋና ኦሜጋ የሆነው አምላካችን ቅድመ ዓለም አስቀድሞ ሲለሠስ ሲቀደስ እንደኖረ ሁሉ ድኅረ ዓለም በፍጥረታቱ ሁሉ ሲመሰገን፣ ሲቀደስና ሲከበር ይኖራል፡፡ ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ የፈጠራቸው መላእክትና ሰውም ይህን ግብር የሚሠሩ ቀደምት ፍጥረታት ናቸው፡፡ (መጽሐፈ አክሲማሮስ ዘእሑድ)
የአምላካችን እግዚአብሔር ምስጋና በሰማይና በምድር ነው፤ በዓለመ መላእክት ዘወትር “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ” እያሉ ከሚያመሰግኑት መላእክት ሁሉ በላይ “አጠንተ መንበሩ” ተብለው የሚጠሩት “ካህናተ ሰማይ” ናቸው፡፡ በምድር ባለች ማኅደረ መለኮት የአምላክ ማደሪያ ቤተ ክርስቲያን ምድራዊ ካህናት በታቦቱ ፊት ማእጠንት እያጠኑ እንደሚያመሰግኑ ሁሉ፣ ቅዱሳን ሱራፌል ሃያ አራቱ ካህናትም የቅድስት ሥላሴን መንበር እያጠኑ ሳያቋርጡ ያመሰግናሉ፡፡
ነቢዩ ኢሳይያስም ስለ እነርሱ ሲናገር እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ንጉሥ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን በረዥምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀምጦ አየሁት፤ የልብሱም ዘርፍ መቅደሱን ሞልቶት ነበር። ሱራፌልም ከርሱ በላይ ቆመው ነበር፥ ለእያንዳንዱም ስድስት ክንፍ ነበረው፤ በሁለት ክንፍ ፊቱን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ እግሮቹን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ ይበር ነበር። አንዱም ለአንዱ፦ ‘ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፣ ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች’ እያለ ይጮኽ ነበር።›› (ኢሳ.፮፥፩-፭) ቅዱስ ዮሐንስ ደግሞ ‹‹በዙፋኑ ዙሪያም ሃያ አራት ዙፋኖች ነበሩ፥ በዙፋኖቹም ላይ ነጭ ልብስ ለብሰው በራሳቸውም የወርቅ አክሊል ደፍተው ሃያ አራት ሽማግሌዎች ተቀምጠው ነበር›› ብሏል፡፡ (ራእይ ፬፥፬)
እነዚህ ቅዱሳን መላእክት ሱራፌል ሥጋ የሌላቸው ረቂቅ የእውነት ካህናት ናቸው፡፡ ከሰማያዊ ሠራዊት ሁሉ ከፍ ከፍም ይላሉ፡፡ የሰው ልጆችን ጸሎት፣ ምጽዋትንና ጽድቅን በልዑል እግዚአብሔር ፊት ያቀርባሉ፡፡ የሚጸለየውን ጸሎትና የሚሠዋውን መሥዋዕት በማዕጠንታቸው እያሳርጉ ሕያዋን ሆነው ይኖራሉ፤ አይሞቱም፤ አይለወጡም፡፡
በከበረች ኅዳር ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን የስማቸው ትርጓሜ ሱራፌል “አጠንተ መንበሩ ለልዑል፣ ኤልሻዳይ” የሆነ ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው፤ አባታችን ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑበት ዕለት ነው፡፡
የቅዱሳን መላአክት ሱራፌል፣ የቅዱሱ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ይደርብን!
ኀዳር ፲፱፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
ጽዮን “”ጸወን” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን “አምባ፣ መጠጊያ” ማለት ነው፡፡ እመ ብዙኀን የሆነችውን የአምላክ እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚገለጽ መሆኑን “ማኅደረ አምላክ” በሚለው ትርጒም እንረዳለን፡፡ ጽዮን የሚለው ስያሜ በቁሙ ለታቦት፣ ለጽላት ሲያገለግል በትንቢታዊ ምሥጢሩ ግን ለድንግል ማርያም፣ ለቤተ ክርስቲያንና ለዘለዓለማዊት ርስተ መንግሥተ ሰማያት ያገለግላል::
ታቦተ ጽዮን “ጽላተ ኪዳን፣ ታቦተ ሕጉ” እየተባለችም ትጠራለች:: “ጽሌ” ማለት “ሰሌዳ” ማለት ሲሆን “ጽላት” ደግሞ በብዙ ቁጥር ነው:: “ኪዳን” ደግሞ በፈጣሪና በሰው ልጆች መካከል ያለ “ውል፣ ስምምነት” ነው፡፡ ታቦተ ጽዮን ዐሥርቱ ቃላት የተጻፈባት በመሆኗ የእግዚአብሔር ሕግጋትን የያዘ ናት፡፡ በዚህም በሕጉ እንድመራ ትእዛዙን እንድፈጽም ያሳስበናል፡፡
አልፋና ኦሜጋ፣ ኤልሻዳይ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር አስቀድሞ ለእስራኤል ሕዝብ ቅድስት የምትሆን ማደሪያውን ታቦተ ጽዮንን በነቢዩ ሙሴ አካማኝነት የሰጣቸው ክብር፣ ሞገስ፣ አምባ እንድትሆናቸው ነው፡፡ (ዘጸ. ፴፩፥፲፰) ለ፭፻ (አምስት መቶ) ዓመት ከእነርሱ ሳትለይ ከአምላክ ጋር መገናኛ፣ በጦርነት ጊዜም ማሸነፊያ ኃይላቸው ሆናም ኖራለች፡፡
ሀገረ እግዚአብሔር የሆነችው ኢትዮጵያም ለከበረች ታቦተ ጽዮን መቀመጫ ለመሆን ታድላለች፡፡ በቀዳማዊው እብነ መለክ፣ እብነ ሐኪም/በቀዳማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት አማካኝነት ወደ ሀገራችን የመጣችው ታቦቷ እስከ አሁን ድረስ በአክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን እንደምትገኝ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይናገራሉ፡፡ (መጽሐፈ ክብረ ነገሥት) የጌታችን ድንቅ ቸርነት የተደረገልን እኛ የድንግል ማርያም የዐሥራት ልጆች የአምላክን ሥራ ልናደንቅና ልናመሰግን ይገባል፡፡
ሀገራችን የገባበትን እንዲሁም አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን የተቀመጠበት ኅዳር ፳፩ ቀንንም ታላቅ በዓልን እናደርጋለን፡፡
የአምላካችን እግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፤ አሜን!
ኀዳር ፲፩፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
አሸናፊና ኃያል፣ ሁሉን ቻይ የሆነ የእግዚአብሔርን ገናንነትና እርሱን የሚመስል አምላክ እንደሌለ የሚያመለክት የስሙ ትርጓሜ “መኑ ከመ አምላክ፤ እንደ አምላክ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?” የሆነ፣ የመላእክት ሁሉ አለቃ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በኅዳር ፲፪ የተሸሞበት ቀን “እግዚኡ ረሰዮ ለውእቱ ሚካኤል እምኵሎሙ መላእክት ይትሌዓል መንበሩ፤ ጌታው ሚካኤልን ከመላእክት ሁሉ መንበሩን ከፍ ከፍ አደረገው” እየተባለ ይከበራል፡፡
የእግዚአብሔር ሠራዊት ሁሉ አለቃ የሆነው መልእኩ ሚካኤል መላእክትን ሁሉ የሚያዝ ነው፡፡ መላእክት ደግሞ አለቃቸውን ያከብራሉ፤ ይታዘዛሉ፤ ከትእዛዙም አይወጡም፡፡ ሳጥናኤል በትዕቢቱ ከክብሩ ተዋርዶ ወደ ምድር ሲጣል አምላክ ቅዱስ ሚካኤልን በእርሱ ፈንታ በዐሥሩ ከተማ በመቶውም ነገደ መላእክት ላይ ሾሞታል፡፡ የእግዚአብሔር ሕዝብ በሆኑት ላይ ጭምርም ሾመው፡፡ “… ዐይኑን አንሥቶ ተመለከተ፤ እነሆም የተመዘዘ ሰይፍ የያዘ ሰው በፊቱ ቆመ፤ ኢያሱም ወደ እርሱ ቀርቦ፤ “ከእኛ ወገን ወይስ ከጠላቶቻችን ወገን ነህ? አለው፡፡ እርሱም “እኔ የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ሆኜ አሁንም ወደ አንተ መጥቼአለሁ” እንዲል፡፡ (ኢያ.፭፥፲፫)
ሠራዊተ መላእክት የሚያከብሩትንና የሚታዘዙለትን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን እኛም እንደ ነቢዩ ኢያሱ እናከብረዋለን፤ እንታዘዘዋለን፡፡ መላእክትን ማክበርና መታዘዝ እንደሚገባ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፡፡ “በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀሁትም ሥፍራ ያገባህ ዘንድ እነሆ እኔ መልአክህን በፊትህ እሰዳለሁ፤ በፊቱ ተጠንቀቁ፤ ቃሉንም አድምጡ፤ ስሜም በእርሱ ስለሆነ ኃጢአት ብትሠሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት፤ አንተ ግን ቃሉን ብትሰማ፣ ያልሁህንም ሁሉ ብታደርግ፣ ጠላቶችህን እጣላቸዋለሁ፣ የሚያስጨንቁህንም አስጨንቃቸዋለሁ፣ መልአኬ በፊትህ ይሄዳልና…፡፡” (ዘጸ.፳፫፥፳-፳፪)
በበዓሉ መታሰቢያ በኅዳር ፲፪ ቀን የክብር ባለቤት በሆነ በእግዚአብሔር ፈቃድ ክንፎቹን ወደ ሲኦል ያወርዳል፤ ኃጥአንንም ወደ አዲሲቱ ምድር ያወጣቸዋል፤ ይኸውም የመላእክት አለቃ የሚካኤል ሠራዊት ይሆናሉ፡፡ ይቅርታ የተደረገላቸውና ምሕረት አግኝተው በአንድ ጊዜ በክንፉ ያወጣቸው ስፍር ቁጥር የላቸውም፡፡ ቅዱስ ሚካኤል በየዓመቱ በኅዳር ፲፪ ቀን እንዲህ እያደረገ እልፍ ነፍሳትን ያወጣል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ወገኖች የሆኑትን ሁሉ እንደ ሥራቸው ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ይወስዳቸዋል፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ አብ መጋረጃ ውስጥ ይገባል፤ በዚህች ዕለት ምድራዊትና ሰማያዊት ስለሆነች ምሕረቱም ከመንበሩ በታች ይሰግዳል፡፡ ስለውኃ ምንጮች፣ ስለ ወይን ቦታዎች፣ ስለ ምድር ፍሬዎች በምድርም ላይ ስለሚኖሩ ስለ ሰው ልጆች ነፍስ ሁሉ፣ ስለ እንስሳትም፣ ስለ ሰማይ ወፎችም፣ ስለ ባሕር ዓሣዎችም፣ በምድር ላይና በባሕር ውስጥ ስለሚንቀሳቀሱ ሁሉ የምሕረት ባለቤት ከሆነ ከአብ ዙፋን በታች ሁልጊዜ በማመስገን ይሰግዳል፤ ልመናውንም እስኪሰማውና የምሕረትንም ቃል እስኪያስተላልፍለት ድረስ ከእግረ መንበሩ ሥር አይነሣም፡፡
ለዚህ ዓለም ምሕረትን የሚለምኑ ቅዱሳን መላእክትም በየዓመቱ ኅዳር ፲፪ ቀን በእግዚአብሔር የዙፋኑ ዐውደ ምሕረት ዙሪያ ተሰብስበው ስለ ሰውና ስለ እንስሳትም ሁሉ ምሕረትን የሚለምን ቅዱስ ሚካኤል ከአብ መጋረጃ ውስጥ በወጣ ጊዜ ቸርና መሐሪ አብ ለቅዱስ ሚካኤል የሰጠው ልብሱን እነዚያ መላእክት ይመለከታሉ፤ ይቅርታን የማግኘት ምልክታቸው ነውና፡፡ ስለዚህ እነዚህ ቅዱሳን መላእክት በምድር ላይ ምሕረት እንደተደረገ ሰውንም እንስሳትንም ይቅር እንዳለ በዚህ ዓለምም የሚሆነውን ሁሉ አይተው ቅዱስ ሚካኤል በለበሰው ልብስ አምሳል ያውቁታል፡፡
መጽሐፈ ስንክሳር እንደሚለው ይህ እጅግ የከበረ ገናና መልአክ ቅዱስ ሚካኤል “ከቅዱሳን ሰማዕታት ጋራ በመሆን ገድላቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ የሚያጽናናቸውና የዘወትር ጠባቂአቸው ሆኖ የሚራዳቸው እርሱ ነው፡፡” የብዙዎቹንም ቅዱሳን ገድል ስንመለከት የዘወትር ጠባቂያቸው ቅዱስ ሚካኤል ነው፡
መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ያደረገውም ተአምር ይህ ነው፡- የእግዚአብሔር ወዳጅ የሆነ ስሙ ዱራታዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፡፡ የሚስቱም ስም ቴዎብስታ ነው፡፡ እነርሱም ሁልጊዜ ያለማቋረጥ የዚህን የከበረ መልአክ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ያደርጉ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ በሀገር ውስጥ ችግር በሆነ ጊዜ ገንዘባቸው አለቀ፡፡ ለቅዱስ ሚካኤልም ለበዓሉ መታሰቢያ የሚያደርጉትን እስኪያጡ ድረስ ቸገራቸው፡፡ ዱራታዎስም ሸጦ ለመልአኩ በዓል መታሰቢያ ያደርገው ዘንድ የእርሱንና የሚስቱን ልብስ ይዞ ወጥቶ ሄደ፡፡
የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም በታላቅ መኰንን አምሳል ለዱራታዎስ ተገልጦ ወደ ባለጸጎች ሄዶ በእርሱ ዋስትና በአንድ ዲናር አንድ በግ እንዲወስድ፣ ሁለተኛም ወደ ባለ ስንዴ ዘንድ ሄዶ በእርሱ ዋስትና ስንዴን እንዲወስድ ዳግመኛም ወደ ዓሣ አጥማጅ ዘንድ ሄዶ አንድ ዓሣ እንዲወስድ ነገር ግን ወደ ቤቱ ሳይርስ የዓሣውን ሆድ እንዳይቀድ አዘዘው፡፡ ዱራታዎስም እንደታዘዘው አደረገ፡፡ ቤቱም በተመለሰ ጊዜ ቤቱ ሁሉ በበረከት ተመልቶ አገኘው፡፡ እርሱም እጅግ ተደስቶ የዚህን የክበር መልአክ የመታሰቢያውን በዓል አደረገ፡፡ ጦም አዳሪዎችንና ድኆችን ጠርቶ አጠገባቸው፡፡
ከዚህም በኋላ ለዱራታዎስና ለሚስቱ ቅዱስ ሚካኤል ሁለተኛ ተገለጠላቸው፡፡ ዱራታዎስንም የዓሣውን ሆድ እንድሰነጥቅ አዘው፡፡ በሰነጠቀውም ጊዜ ፫፻ (ሦስት መቶ) የወርቅ ዲናር በዓሣው ሆድ ውስጥ ተገኘ፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ዱራታዎስንና ሚስቱን ቴዎብስታን እንዲህ አላቸው፤ “ከዚህ ዲናር ወስዳችሁ ለባለ በጉ፣ ለባለ ዓሣውና ለባለ ስንዴው ዕዳችሁን ክፈሉ፡፡ የቀረውም ለፍላጎታችሁ ይሁናችሁ፤ እግዚአብሔር አስቧችኋልና በጎ ሥራችሁን፣ መሥዋዕታችሁንና ምጽዋታችሁን አስቦ በዚህ ዓለም አሳመረላችሁ፤ በኋለኛውም መንግሥተ ሰማያትን አጀጋጀላችሁ” አላቸው፡፡
እነርሱም ይህን ነገር ሲሰሙ ደነገጡ፡፡ የከበረ ገናናው መልአክም “ከመከራችሁ ሁሉ ያዳንኳችሁ የመላእክት አለቃ እኔ ሚካኤል ነኝ፤ መሥዋዕታችሁንና ምጽዋታችሁን ወደ እግዚአብሔር ፊት ያሳረግሁ እኔ ነኝ፡፡ አሁንም በዚህ ዓለም ከበጎ ነገር እንድታጡ አላደርጋችሁም” አላቸው፡፡ ይህንንም ከነገራቸው በኋላ ወደ ሰማያት ወጣ፡፡ እነርሱም በፍርሃትና በክብር ሰገዱለት፡፡
የመላእክት ሁሉ አለቃ የቅዱስ ሚካኤል ጥበቃው፣ ጸሎቱ፣ አማላጅነቱና ተራዳኢነቱ አይለየን፤ ከበዓሉ ረድኤት በረከት ይክፈለን፤ አሜን!
(ምንጭ፡– ድርሳነ ቅዱስ ሚካኤል፣ መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ኅዳር)
ኀዳር ፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
አዘክሪ ድንግል አዘክሪ
ለልጅሽ አሳስቢ አዘክሪ
ለኃጥአን ለምኝልን
አይደለም ለጻድቃን
ከጠላት ሸሽተሽ ለተሰደድሽበት
በግብጽ በረኀ በሙቀቱ ውዕያት
በዱር በገደሉ በቁር ግሽበት
በጀርባዎችሽ አዝለሽ ለተጓዝሽበት
በመታቸው ተረከዞች እንቅፋት
ያን ሁሉ መከራ ለተቀበልሽበት
ለማዳን ሰውን ከጽኑ ግርፋት
ከሲኦል ትላትል ቁንጥጫ ከገሃነመ እሳት
ለአዳም ዘር በሙሉ የነፍስ ድኅነት
ለምኝልን እናት አትተይን በእውነት
አዘክሪ ድንግል አዘክሪ
ለልጅሽ አሳስቢ አዘክሪ!
በመዝሙርና ሥነ ጥበባት ክፍል
ጥቅምት ፳፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
ልዑል ሆይ ክንድህን ስደድ
ናማ ውረድ
ና ተወለድ
ብለው ነቢያት በጾም ጸሎት ተጉ ጮኹ!
ጨለማውን አስወግዶ ብርሃኑን ያበራልን
አንጠፋ ዘንድ በፍጹም ፍቅር የራራልን
በግብዞች በአይሁድ ሥርዓት
በሕጋቸው እንደጻፉት
የሾህ አክሊል ተቀዳጅቶ
መጻጻውን ተጎንጭቶ
…..
እርሱ ሞተ ሊሰጥ ሕይወት
ወየው በሉ አልቅሱለት፤
የእጁን መዳን ያገኛችሁ የጌንሴሬጥ ድውይ ሁሉ
ለኢየሱስ አልቅሱለት፤ ፍዳን ስላያት በመስቀሉ
የ፲፪ ዘመን ሥቃይ በልብሱ ጫፍ ………
በቅጽበት ውስጥ የጠፋልሽ
ተገረፈ፤ ተንገላታ፤ የማይሞተው ሞትን ሞተ፤ ……..
ያ ርኅሩኅ ቸር መዳኒትሽ
ኢያሮስ የት ነው ያለህ!
ያ’ዓለም ጌታ ተተፋበት ሴት ልጅህን ያዳነልህ!
እመቤቴ የልጅሽን መከራውን እንዴት ቻልሽው አልልሽም
ቅዱስ ዳዊት በእሳት ፈረስ ሰባቱ ኃያል …..
መላእክቱ ካንቺ መጥተው ቢያፅናኑሽም
ለሦስት ቀን የአንዱ ልጅሽ ከሞቱ ይልቅ አሟሟቱ ….
እያስነባሽ እህል ውኃ እንኳን አልቀመስሽም
አብ ሆይ ማረን!
መንፈስ ቅዱስ ተዘከረን!
በልጅህ ደም የተገዛን ለመሆኑ አላወቅንም ዋጋችንን
ጽድቃችንም የመርገም ጨርቅ ከንቱ ሆኖ
መኖሪያችን በሲኦል ቋት ተወስኖ
ለዘመናት ስንገረፍ በእሳት ላንቃ
ያበቃ ዘንድ ይህ እንግልት ይህ ሰቆቃ
እሰይ እሰይ ይኸው አሁን የምሥራች
የሞት ዐዋጅ ተሻረልን፤ ገነት ዳግም ተከፈተች
የጥሉ ግድግዳ ፍርሶ ሰላም ሆኗል ከላይም ከታች
፶፻፭፻ የንስሐ የጣር ዘመን ተፈፀመ
በደላችን ተሰርዞ በክርስቶስ ደም ታተመ::
ጥቅምት ፳፬፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
በዐሥራ ሦስተኛው ክፍለ ዘመን በሮሜ ሀገር የተወለዱት ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብ የስማቸው ትርጓሜ “የብዙኀን አባት” አንድም ቡላ ማለት “የተወደደ፣ እግዚአብሔር የተለየ” ነው፡፡ መጽሐፈ ስንክሳር ታላቅና ክቡር የሆነ አቢብ የተባለ መስተጋድል አባ ቡላ ተብሎም የሚታወቅ አባት በከበረች ዕለት ጥቅምት ሃያ አምስት (፳፭) እንዳረፈ ይጠቅሳል፡፡
አስቀድሞም ከሃዲው ንጉሥ መክስምያኖስ ክርስቲያኖች ላይ ባመጣባቸው ስደት ምክንያት አባትና እናታቸው አብርሃምና ሐሪክ ተሰደው ሲኖሩ ልጅን ባማጣታቸው በጸሎትና በጾም አምላካቸው እግዚአብሔርን በመለመናቸው መልአክ ለአብርሃም ተገልጾ “ይህ ፍሬ የአንተ ነው፤ እርሱም ወደ እኔ የሚቀርብ እግዚአብሔርን የሚያስደስት ፈቃዱንም የሚፈጽም የአመረ መባዕ ነው” በማለት እግጅ መልካም ፍሬን ሰጠው፡፡ ደጉ ሰው አብርሃምም ከእንቅልፉ ነቅቶ ለሚስቱ በሕልሙ ያየውንና መልአኩ የነገረውን ሁሉ ነገራት፡፡ እርሷም ደስ ተሰኘች፤ ሁለቱም በአንድነት እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ የአብርሃም ሚስት ሐሪክ በፀነሰች ጊዜም በቤታቸው አደባባይ ሁለንተናው መልካምና ታላቅ ዛፍ በቀለ፡፡ በቅጠሉም ላይ በዕብራይስጥ ቋንቋ የተጻፈ “በጽዮን አድሮ የሚኖር የያዕቆብ ፈጣሪ የእግዚአብሔር አገልጋይ ቡላ” የሚል ጽሕፈት አገኙ፡፡ በዚህም ጊዜ በተአምሩ ተደንቁ፡፡
ቀጥሎም መልኩ ያማረ ከብርሃናት ይልቅ ፊቱ የሚያበራ ወንድ ልጅን ወለደች፡፡ ከዚህም በኋላ ለአንድ ዓመት ያህል ክርስትናን ሳይስነሡ ሲያኖሩት እመቤታችን ድንግል ማርያም ለሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ለሰለባስትሮዮስ ተገልጣ ወደ አብርሃም ቤት በመሄድ ሕፃኑን እንዲያጠምቀው ስላዘዘችው የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው፡፡ ስሙንም “ቡላ” ብላ ሰየመው፤ ወላቹም በዚህን ጊዜ አደነቁ፡፡ ጸሎትም አድርጎ የቊርባን ኅብስትና ወይን የተመላ ጽዋ ከሰማይ ስለወረደ ቀድሶ ቅዱስ ሥጋውንና ደሙን ሕፃኑንና ወላጆቹን አቀበላቸው፡፡ በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ የአንድ ዓመት ልጅ ሲሆን “በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ አብ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው፤ በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ ወልድ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው፤ በባሕርይ በህልውና በመለኮት በአብ ከወልድ ጋር አንድ የሆነ መንፈስ ቅዱስ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው” ብሎ ተናገረ።
ጥቂት ዓመታት ካለፉም በኋላ በኅዳር ሰባት ቀን አባቱና እናቱ ዐረፉ፤ ሕፃን ቡላ ዐሥረኛው ዓመቱ ላይ ሌላ መከራ አጋጠመው፤ ሕዝቡን ለጣዖት መስገድ የሚያስገድድ መኮንን እንደመጣ በሰማ ጊዜም ሕፃኑ በፊቱ ቀርቦ የረከሱ ጣዖታትን ረገመ፡፡ በአካል ትንሽ መሆኑን የተመለከተው መኮንኑ ለጊዜው ቢያደንቅም በችንካር ቸንክረው፣ ሥጋውን ሰነጣጥቀው፣ ቆዳውንም ከአጥንቱ እንዲገፉት፣ እጁቹንና እግሮቹን በመጋዝ እንዲቀርጡ፣ በሶሾተልና በጦሮች አድርገው ከመንኮራኩር ውስጥ እንዲጨምሩት፣ ዳግመኛ በመንገድ ላይ እንዲጎትቱት አዘዘ፡፡ ሆኖም መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ ስላዳነው ያለ ጉዳት ጤነኛ ሆነ፡፡ ቅዱሱ ሕፃን ቡላ ግን ሌላ መኮንን ጋር ሄዶ የረከሱ ጣዖታትን ገረመ፡፡ በዚህም ጊዜ መኮንኑ ተቆጥቶ ሚያዝያ ወር በባተ በዐሥራ ስምንተኛው ቀን ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ ስላዘዘ ቆረጡት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ከሰማይ ወርዶ ከሞት አስነሣው፡፡ በዚህም ጊዜ የመነኮስ ልብስንና አስኬማን በመስቀል ምልክት አለበሰውና እንዲህ አለው፤ “ከቅዱሳንና ከጻድቃን አንድነት ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አዝዞአል፡፡”
ቅዱስ አባታችንም በዚህ ጊዜ ከደረቅ ተራራ ላይ ወጥተው በውስጧ እየታገደሉ ሲኖሩ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራ መስቀል በማሰብ ከረጅም ዕንጨት ላይ በመውጣት ራሳቸውን ወደታች ሁል ጊዜ ይወረውሩ ነበር፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀንም በዛፍ ላይ ሲወረወሩ ሰይጣን በቅናት ተነሣስቶ ገደላቸው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አነሣቸውና “ከእንግዲህ ስምህ ቡላ አይሁን፤ አቢብ ይባል እንጂ፤ የብዙዎች አባት ትሆናለህና” አላቸው፡፡
ከዚህ ቀጥሎ አቡነ አቢብ የክርስቶስን ፍቅር በመጨመር ፊታቸውን ይጸፉ፣ ሥጋቸውን በጥቂት ይቆርጡ፣ ጀርባቸውን ሰባት ጊዜ ይገርፉ ነበር፡፡ ጌታችን በዚህ ጊዜም ከእርሳቸው ሳይለይ ይፈውሳቸው ነበር፡፡ በየእሑድም ቀን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም እንደተወለደ፣ በሌሎች ቀኖችም እንደተያዘና ከአይሁድ መከራ እንደ ተቀበለ ሁኖ ይገለጽላቸው ነበር። በዚህም የተነሣ ለአርባ ሁለት ዓመታት ምግብ ሳይበሉና ውኃ ሳይጠጡ ከኖሩ በኋላ ለዐሥራ ሁለት ወር በራሳቸው ተተክለው ሲኖሩ ናላቸው ፈስሶ አለቀ፡፡
የጌታችንን መከራ በአሰቡ ጊዜ በአንዲት ቀን ሰይፉን በአንጻሩ ተክለው ከዕንጨት ላይ በመውጣት በላዩ ወድቀው ሞቱ፤ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም ከአእላፍ መላእክት ጋር መጥታ “የእኔና የልጄ ወዳጅ ሰላምታ ይድረስህ” አለችው። ከበድኑም ቃል ወጥቶ “የሰማይና የምድር ንግሥት እመቤቴ ሰላምታ ይገባሻል” አላት፡፡ እርሷም በከበሩ እጆቿ ዳሥሣ ከሞት አስነሣቸው።
ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብ ከዚህ ዓለም ድካም የሚያርፉበት ጊዜ ሲደርስ ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በእጁ ልዩ የሆኑ አክሊሎችን የሚያበሩ ልብሶችንም ይዞ ተገለጠለትና እንዲህ አላቸው፤ “ወዳጄ አቢብ ሆይ፥ በማያልቅ ተድላ ደስታ ደስ አሰኝህ ዘንድ ወደ እኔ ና፤ ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ እኔ ኃጢአቱን አስተሠርይለት ዘንደ በራሴ ማልኩልህ፤ ወይም ለተራቆተ የሚያለብሰውን፣ ለተራበም የሚያጠግበውን፣ ለተጠማ የሚያጠጣውን፣ የገድልህን መጽሐፍም የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውንና የሚሰማውን፣ በጸሎትህም የሚታመኑትን ሁሉ እስከ ዐሥር ትውልድ እምራቸዋለሁ፤” ይህንም ብሎ አፋቸውን ሳማቸው፤ በደረቱም ላይ አድርጎ ወደ አየር አወጣቸው፤ የመላእክትንም ምስጋና በሰማች ጊዜ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች፤ ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ገባች።
እነሆ ሰማዕቱ አቡነ አቢብ ምእመናን በሚቀምሱት የዕለት ምግብ አማካኝነት በነፍስም በሥጋም እንዲድኑ አስገራሚ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደተቀበሉ የሚናገር የገድል ተአምራታቸው ይህ ነው፡- ብዙዎች ስማቸውን ጠርተው በሚቀምሱት ምግብ አማካኝነት ከተለያዩ በሽታዎች የተፈወሱ አሉ፡፡ ይህ ቃል ኪዳናቸው ለሁላችን ይደረግልን ዘንድ ከመመገባችን አስቀድሞ የእግዚአብሔርን ስም እንጥራ (አቡነ ዘበሰማያትን ማለቱ ነው፡፡) ከተመገብን በኋላም የዕለት ምግባችንን ስለሰጠን እግዚአብሔርን እናመስግን፡፡ ዘወትር ከተመገብን በኋላ ሦስት ጊዜ ‹‹ስለ ወዳጅህ ስለ አቡነ አቢብ›› እያልን ሦስት ጊዜ እንቅመስ፡፡ አስቀድሞ ጌታችን መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአቡነ አቢብ ተገልጦላቸው ‹‹…ወዳጄ አቢብ ሆይ! የሰውን ልጅ ለማዳን የተቀበልኩትን ሕማማተ መስቀል እያሰብህ ይህንን ሁሉ ገድል ፈጽመሃልና ምን እንዳደርግልህ ትወዳለህ?›› አላቸው፡፡ ንዑድ ክቡር ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብም ‹‹ጌታዬ አምላኬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! መቼም ሰው ሁሉ ሳይመገብ አይውልም፤ አያድርምና በተመገበ ጊዜ ስሜን ጠርቶ የተማጸነውን ማርልኝ›› አሉት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አባታችን አቡነ አቢብ ለሰው ልጆች ያላቸውን ፍቅር ካደነቀ በኋላ ‹‹…ከማዕድ በኋላ ስብሐት ተብሎ የተረፈውን ‹በእንተ አቢብ› ብሎ ሦስት ጊዜ የተመሰገበውን ሰው ሁሉ እምርልሃለሁ›› በማለት ታላቅ የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡
ያልተጠመቀ አረማዊ አሕዛብም እንኳን ቢሆኖ ‹‹ስለ አቡነ አቢብ›› ብሎ ከተማጸነ ጌታችን ያንን ሰው ወደ ቀናች የእምነት መንገድ ሳይመራወና በንስሓ ሳይጠራው በሞት እንደማይወስደው ለአባታችን ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ለማዳን ትንሽ ምክንያትን የሚፈልግ ያለ ምክንያትም የማያድን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ እስከ ዘለዓለም ድረስ ይክበር ይመስገን! ሰው ተመግቦ እንኳን መዳን እንዲችል ይህን ድንቅ ቃል ኪዳን ለአባታችን ሰጥቷቸዋልና በየቀኑ በዚህ ቃል ኪዳን እንጠቀምበት፡፡ ተመግበን ከጨረስንና ስብሐት ካልን በኋላ ሦስት ጊዜ ‹‹በእንተ አቡነ አቢብ›› ብለን እንቅመስ፡፡ በጥቅምት ፳፭ ቀን በዓመታዊ የዕረፍት በዓላቸው ታስበው የሚውሉት ጻድቁና ሰማዕቱ አቡነ አቢብ የቃል ኪዳናቸው ረድኤት በረከት ይክፈሉን!
(ምንጭ፡– ደብረ ሰላም ቃጭልቃ አቡነ አቢብ ገዳም ያሳተመው ገድለ አቡነ አቢብ፣ ገጽ ፻፭)
በእንተ ቅዱሳን ኀሩያን)
ጥቅምት ፲፯፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
ርእሰ ዲያቆናት ወቀዳሚ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ የሹመቱ መታሰቢያ ጥቅምት ፲፯ ነው፡፡ ከሰባቱ ዲያቆናት መካከል ቀዳምት የሆነው ቅዱሱን የመረጡት እራሳቸው ሐዋርያት ናቸው፡፡ የስሙ ትርጓሜ “ፋና፣ አክሊል” የሆነ የእግዚአብሔር ልዩ ባለሟል፣ አጋእዝተ ዓለም ሥላሴን በክብሩ ለማየት የበቃ ሰማዕትም ነው፡፡
ፍጹም እምነት ያለው፣ መንፈሳዊ ቅናትን የተመላ እንዲሁም ተአምር የማድረግ ጸጋ የነበረው ቅዱስ ነበረ፡፡ በዘመኑ የሚያስተምራቸው ትምህርቶችም ሆነ ንግግሮቹ መንፈስ ቅዱስ የመላባቸው ስለነበሩ በመቃወም ይከራከሩት የነበሩትን ሁሉ መልስ አሳጥቶአቸዋል፡፡ በዚህም ነበር በቅንአት ተነሣሥተው በሐሳት ምስክር የከሰሱት፡፡ በኋላም ተፈርዶበት በድንግይ ተወግሮ የሰማዕትነትን አክሊል በተወለደበት ዕለት ጥር አንድ ቀን ተቀብሎአል፡፡
የቅዱስ እስጢፋኖስ ጸሎት፣ አማላጅነት እና ተራዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ያሳተፍን፤ አሜን!
ጥቅምት ፲፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
በከበረች ጥቅምት ፲፬ ቀን አቡነ አረጋዊ ተሠወሩ፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመጡት ቅዱስ አባታችን ዘጠኙ ቅዱሳን የእግዚአብሔር አገልጋዮችን ኢትዮጵያ እስኪደርሱ ድረስ በመንገድ የመሯቸው እርሳቸው እንደሆኑ መጽሐፈ ስንክሳር ይገልጻል፡፡
የዘንዶ ጅራት በመያዝ ከደብረ ዳሞ ተራራ ላይ የወጡት፣ በዚያም ፍጹም ገድላቸውን የፈጸሙት ቅዱስ አባታችን አቡነ አረጋዊ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ስማቸውን ለሚጠራና መታሰቢያቸውን ለሚያደርግ እንደሚማርላቸውም ተነግሯቸዋል፡፡
ከመምህራቸው ከአባ ዻኩሚስ በተማሩት መሠረትም ለልጆቻቸው መነኰሳት ሥርዓተ ማኅበርን ሠርተውላቸዋል፡፡ ከዚያም በእግዚአብሔር ቸርነት እንደ ነቢያቱ ሄኖክና ኤልያስ ከዚህ ምድር ተሠውረዋል፡፡
የቅዱስ አባታችን አቡነ አረጋዊ ጸሎት፣ አማላልጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!!!
ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ጥቅምት ፲፬
