ሕፃኑ ሰማዕት

ጥር ፲፬፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ግብዝና ደካማ የሆነው የሰውን ሥጋ አሸንፎ፣ መከራን ተቀብሎ፣ ችግርን ተቋቁሞ፣ ፈተናን አልፎ መንፈሳዊ ሕይወትን ለመኖርና ክርስቲያን ለመሆን የሚደረገው ትግል እራሱን የቻለ ተጋድሎ እንደሚያስፈልገው የታወቀ ነው፡፡ እውነተኛ ለሆነው የክርስትና እምነተና ኦርቶዶክሳዊ ሃይማኖት የሚከፈለው መሥዋዕትም የተለየ ስፍራ አለው፡፡

እሳት ሰንሰለቱን ሳይፈሩ፣ እራሳቸውን እጅግ ለበዛ ሥቃይ አሳልፈው የሚሰጡ ሰማዕታት የተለየ ክብር አላቸው፡፡ ፍጹም በሆነው የክርስቶስ ፍቅር ዓለም የሚያመጣባቸውን መከራ ለመቀበል በሙሉ ፈቃደኝነት ቆርጠው ተነሥተው ከአላውያን ነገሥታት አልያም ከመኳንንቶች ደግሞም ከከሃድያን ደርሰው በግልጽ ለእውነተኛው ጌታ በመመስከር እውነተኛ ምስክሮች ይሆናሉ፡፡

ከሁሉም የሚደንቀው ደግሞ ከእሳት ምድጃ ቢጥሏቸው፣ ከፈላ ውኃ ውስጥ ቢጨምሯቸው፣ ለአንበሳ እና አውሬ መብል አሳልፈው ቢሰጧቸው እምነታቸው ምንም አለመቀየሩ ነው፡፡ ለሚያምኑበትና ለሚመኩበት ኃይል ብርታት የሚሆን፣ መሐሪና ይቅር ባይ አምላካችን  ጻድቃንን ቅዱሳንን ሰማዕታት ለጠላት አሳልፎ የማይሰጥ ነውና መላእክቱን ልኮ ውኃውን እንደ ውርጭ የሚያቀዘቅዝ፣ እሳቱን ውኃ የሚያደርግ፣ የተራቡ አራዊት የቅዱሳንን እግርና እጅ እንዲልሱ የሚያደርግ ነው፡፡ ዳግመኛም ለልዩ ልዩ ለሥቃይ አሳልፈው ቢሰጧቸውም የክብር ባለቤት እራሱ ከሰማየ ሰማያት ከእልፍ አላፋት መላእክት ጋር ወርዶ እንዳጽናናቸው እንዲሁም እንዳጸናቸው ገድላቸው ይናገራል፡፡ (ገድለ ቅዱሳን)

በከበረች ሐምሌ ፲፱ ቀን የጌታችን ዕጹብ ድንቅ ሥራ በተገለጠባት ዕለት የሚያስደንቅ ገድል ያደረገ የሦስት ዓመቱ ሕፃን ቅዱስ ቂርቆስ ገድልም ፍጹም ድንቅ ነው፡፡ በዚህች ቀን በፈላ የጋን ውኃ ውስጥ ቅዱሳኑ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ ‹‹እናቴ ሆይ አትፍሪ›› እያለ ያረጋጋትና በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ ውኃውም እንደ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡ ይህንም ያደገረው የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

የዘመኑ የአረማዊው መኰንን የእለእስክንድሮስ ወታደሮች ከሮም ወደ ወደ ተርሴስ ከእናቱ ጋር ሸሽቶ የገባውን ሕፃኑ ሰማዕት ይዘው ፈጣሪን ክዶ ከጣዖት እንዲሰግዱ በዓይነቱ ቢያሠቃዩትም ስላልተቀበላቸው በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡ አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡ እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲሆን፣ መኰንኑ በተአምራቱ ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡

ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ አስገብተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜ ቅዱስ ገብርኤል አድኗቸዋል፡፡ በመጨረሻም ሕፃኑ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብሎ ጥር ፲፭ ቀን አንገቱ ተቆርጦ የሰማዕትነት አክሊል ተቀብሏል፡፡ በተመሳሳይም እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ሰማዕት ሆናለች፡፡ ግሩምና ድንቅ የሆነው የሰማዕታት ገድል የሁላችንም አስተማሪና አስማሪ ነው፡፡ በእነርሱ ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት የእኛ ኃጢአት ይስተሠረይልናልና፡፡

የቅዱሳኑ ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ጥር፣ ፲፭ ቀን

 

 

 

የቃና ዘገሊላ ሰርግ

ጥር፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ዲያቆን ወልዳይ መረሳ

በአዲስ ኪዳን የዮሐንስ ወንጌል ላይ እንደተጠቀሰው ዶኪማስ ሰርግ ባደረገበት ወቅት ድንግል ማርያምና ጌታ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር የታደሙባት (ዮሐ ፪፥፩-፲፩ )፣ እንዲሁም የሐዋርያው ናትናኤል የትውልድ ሀገር ገሊላ ናት (ዮሐ ፳፩፥፪ )። ጌታ በዚሁ ስፍራ ሆኖ በመናገር በቅፍርናሆም ታሞ የነበረውን የሹሙን ልጅ ከሕመሙ ፈውሶታል። (ዮሐ ፬፥፵፫-፶፬ )

ቤተ ክርስቲያን በዓላትን በቅዱሳን ስም፣ በዕለቱ በተፈጸመው ድርጊት ወይም በቦታ ስም ትሰይማለች። ይህም “በአዳሪው ስም ማደሪያው ይሰየማል” እንደሚባለው እንጂ፣ ተአምራቱን የፈጸመው ራሱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

ቤተ ክርስቲያንም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረትን ተከትላ ጌታ ለገለጠበት ስፍራ ክብርና ቅድስና በመስጠት በዓሉን በቦታው ስም “ቃና ዘገሊላ” ብላ ታከብራለች። (ዘጸ.፫፥፭፣ ፪ ጴጥ. ፩፥፲፰) ምንም እንኳን በቃና የተደረገው ተአምር ጌታ ተጠምቆ በቆሮንቶስ ገዳም ከተፈተነ በኋላ በየካቲት ወር የተፈጸመ ቢሆንም የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ግን “የውኃውን በዓል ከውኃ በዓል ጋር” በማዛመድ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ከጥምቀት ማግስት እንዲከበር አድርገዋል።

በዚህም መሠረት የቃና ዘገሊላ በዓል ከዘጠኙ የጌታ ንኡሳን በዓላት አንዱ ሆኖ ከዋዜማው ጀምሮ በዝማሬና በቅዳሴ በድምቀት ይከበራል። በዕለቱ የሚቀርቡት ንባባትና ዜማዎችም በቃና ዘገሊላ የተደረገውን ተአምርና ምሥጢር የሚዘክሩ ናቸው። ቤተ ክርስቲያናችን በዛሬው ዕለት የምታቀርባቸው ዝማሬዎችና የቅዱስ መጽሐፍ ንባባት በአንድ ዋና ነጥብ ላይ ያተኩራሉ፤ ይህም በቃና ዘገሊላ የተከናወነው የመጀመሪያው ተአምርና በውስጡ የያዘው ጥልቅ ምሥጢር ነው። ይህ ታሪክ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፪ ከቁጥር ፩-፲፩ ላይ በስፋት ተመዝግቦ ይገኛል። ምንም እንኳን የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት የዚህን ወንጌል ትርጓሜ እጅግ ረቂቅና ሰፊ በሆነ ምሥጢር ቢተነትኑትም፣ እኛ ግን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድና እንደ አቅማችን መጠን እነርሱ ካስተማሩት ጥቂቱን እንደሚከተለው በአጭሩ እንመለከታለን።

 የቃና ዘገሊላ ሰርግ

በሦስተኛው ቀን በገሊላ ቃና ሰርግ ነበር፤ የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች። ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱም ወደ ሰርጉ ታደሙ። የወይን ጠጅ ባለቀ ጊዜ እናቱ “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” አለችው። እርሱም “አንቺ ሴት፣ ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም” አላት። እናቱም አገልጋዮቹን “እርሱ የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ” አለቻቸው። በዚያም እንደ አይሁድ ሥርዓት ለመንጻት የሚሆኑ ስድስት የድንጋይ ጋኖች ነበሩ። ኢየሱስም “ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው” አላቸው፤ እስከ አፋቸውም ሞሏቸው። “አሁን ቀድታችሁ ለሰርግ አዘጋጁ (ለአሳላፊው) ስጡት” አላቸው።አሳላፊውም ወደ ወይን የተለወጠውን ውኃ በቀመሰ ጊዜ ከወዴት እንደመጣ አላወቀም፤ ውኃውን የቀዱት አገልጋዮች ግን ያውቁ ነበር። አሳላፊውም ሙሽራውን ጠርቶ “ሰው ሁሉ አስቀድሞ መልካሙን ወይን ያቀርባል፣ ከጠጡ በኋላ ግን የተለወጠውን (መካከለኛውን) ያቀርባል፤ አንተ ግን መልካሙን ወይን እስከ አሁን አቆይተሃል” አለው።

ኢየሱስ ይህን የመጀመርያ ተአምር በገሊላ ቃና አደረገ፤ ክብሩንም ገለጠ፤ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ። (ዮሐ ፪፥፩-፲፩) በዚህ ቅዱስ ሰርግ ላይ የጌታ ትሕትና ተገልጦበታል፤ ክብሩ ታውቋል፤ የድንግል ማርያም ርኅራኄና አማላጅነት ታይቷል፤ የጋብቻ (የምሥጢረ ተክሊል) ክብርም በተግባር ትምህርቱ ተሰጥቶበታል።

የጌታ ትሕትና መገለጥ

ክርስቶስ በቤተልሔም በከብቶች ግርግም ተወልዶ፣ በዮርዳኖስም በባሪያውና በአገልጋዩ በዮሐንስ እጅ ተጠምቆ የትሕትና አባት መሆኑ በሁሉ ዘንድ የታወቀ ነው። አሁን ደግሞ “ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ (ድሀ አደረገ)” ተብሎ እንደተጻፈው፤ (ፊል ፪፥፯) በፍጥረታቱና በባሪያዎቹ ሠርግ ላይ እንደ ዋና የክብር እንግዳ ሳይሆን እንደ ማንኛውም እንግዳ ተገኘ። ያውም የወይን ጠጅ እንኳ ለታዳሚዎቻቸው በማያበቃቸው በድሆች የሰርግ ቤት ተገኘ።

ማንንም ሳይንቅ ከባሪያዎቹ ጋር እንደ አንዱ ታዳሚ ተቀመጠ። ያንን ታላቅ ተአምርም “እዩልኝ ስሙልኝ” ሳይል፣ ወይን በሚቀመጥበት በዚያ በጓዳ ጋኖቹ ዘንድ አደረገው። ይህም በሉቃስ ወንጌል (፲፬፥፯-፲፩) ላይ “አንድ ሰው ለሰርግ ቢጠራህ ከሁሉ በላይ ባለው የክብር ቦታ አትቀመጥ፤ ምናልባት ከአንተ ይልቅ የሚከበር ሰው ተጠርቶ ከሆነ፣ አንተንና እርሱን የጠራው መጥቶ ‘ለዚህ ሰው ስፍራ ልቀቅለት’ ይልሃል፤ ያን ጊዜም እያፈርህ ወደ መጨረሻው ስፍራ ትወርዳለህ። ነገር ግን በተጠራህ ጊዜ ሄደህ በዝቅተኛው ስፍራ ተቀመጥ፤ የጠራህ ሰው መጥቶ ‘ወዳጄ ሆይ፣ ወደ ላይ ከፍ በል’ ባለው ጊዜ፣ አብረውህ በተቀመጡት ፊት ክብር ይሆንልሃል። ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና፤ ራሱንም ዝቅ የሚያደርግ ከፍ ይላል” ብሎ ራሱ ያስተማረውን ትምህርት በተግባር የፈጸመበት አርአያነት ነው። በዚህም እኛ እንዴት በትሕትና፣ ለሰው ታይታ ሳይሆን ከልብ ማገልገል እንዳለብን አስተማረን።

ክርስቶስ ማንነቱን መግለጡ

በቃና ሰርግ ቤት የተደረገው ተአምር የአዳዲስ አማኞችንና የሐዋርያትን እምነት ለማጽናትም የተደረገ በመሆኑ፣ ወንጌላዊው ዮሐንስ “ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ” ይለናል። እመቤታችን ድንግል ማርያምም ጌታችን ማንነቱ የሚገለጥበት ጊዜ መድረሱን አውቃ “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” አለችው። ጌታችንም “ጊዜዬ ገና አልደረሰም” ማለቱ፣ በወቅቱ ያልነበረው ይሁዳ መጥቶ ተአምሩን እንዲያይና ለወደፊት “እኔ በሌለሁበት ተአምር አድርጎ ለየኝ” የሚል ምክንያት እንዳይኖረው ለማድረግ እንደሆነ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ተርጒሞታል።

የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ ክብርና ርኅራኄ ወንጌላዊው ሲገለጽ ቅዱስ ዮሐንስ ታሪኩን ሲጀምር “የኢየሱስ እናት በዚያ ነበረች” በማለት ክብሯን ይገልጻል። ወንጌላዊው በየትኛውም ስፍራ ስሟን በቀጥታ ከመጥራት ይልቅ “እናቱ” ወይም “የኢየሱስ እናት” እያለ ይጠራታል፤ ይህም ሐዋርያት ለእመቤታችን ያላቸውን ታላቅ አክብሮትና ድንግል ማርያም ያላትን የአምላክ እናትነት ጸጋ የሚያስረዳ ነው። ጌታችንም እናቱን “አንቺ ሴት” ማለቱ፣ አዳም ሔዋንን “ከአጥንቴ አጥንት ከሥጋዬ ሥጋ ናት” (ዘፍ ፪፥፳፫) እንዳላት ሁሉ፣ እርሷም የጌታ የሥጋዌው (የሰው የመሆኑ) ምክንያት መሆኗን ለማረጋገጥ ነው።

ድንግል ማርያም የወይኑ ማለቅ በሰርገኞቹ ላይ የሚያመጣውን ኃፍረት ተረድታ፣ እነርሱ ሳይጨነቁና ሳይጠይቋት ቀድማ በመለመን ርኅራኄዋን ገልጻለች። ጌታችንም የእናቱን ልመና ሰምቶ ውኃውን ወደ ወይን በመለወጥ ተአምሩን ፈጸመ።

ምሥጢረ ተክሊል

ጋብቻ ቅዱስ መሆኑ ይታወቅ ዘንድ ክርስቶስ ከእናቱና ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በሰርጉ ላይ ተገኝቷል። ክርስቶስ የቤተ ክርስቲያን ራስ ነው፤ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ የታነጸች ናት። ይህ ምሥጢርም በእግዚአብሔር ፊት፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ የሚፈጸም መሆኑን ያስረዳል። ጌታችን በሰርግ ቤት እመቤታችንን “አንቺ ሴት” ብሎ መጥራቱ አዳም ሔዋንን “ከአጥንቴ አጥንት፣ ከሥጋዬ ሥጋ ናት” (ዘፍ ፪፥፳፫) እንዳላት ሁሉ፣ ስለ ሥጋዌው (ሰው ስለመሆኑ) የሚጠቁም ነው። ውኃውን ወደ ወይን መለወጡም የከበረ ደሙ ምሳሌ ነው። ስለሆነም ምሥጢረ ተክሊል በሥጋውና በደሙ የሚከብርና አንድ ጊዜ ብቻ የሚፈጸም ቅዱስ ሥርዓት ነው።

የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር በረከቱንና ረድኤቱን ያብዛልን። የአምላክ እናት ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም በአማላጅነቷ አትለየን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

 

 

በዓለ ጥምቀት

ጥር፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 በጥር ዐሥራ ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአጥማቂው ቅዱስ ዮሐንስ ዘንድ በዮርዳኖስ ወንዝ ውኃ ተጠመቀ።

ይችህም ዕለት በዮናኒ ቋንቋ ኤጲፋንያ ትባላለች፤ ትርጓሜውም “መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው።” ልዩ የሆነች የሦስትነቱን ምሥጢር ገልጦባታልና አብ ከሰማይ ሆኖ “የምወደው በርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” እያለ ሲመሰክር ወልድም በዮርዳኖስ ወንዝ ቁሞ ሳለ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል በወልድ ራስ ላይ ሲቀመጥ ይህ አጥማቂው ዮሐንስ እንደመሰከረ።

እንዲህ ሲል “ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተጠምቆ ከውኃ በወጣ ጊዜ ወዲያውኑ ሰማይ ተከፈተ፤ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በጌታችን ራስ ላይ ተቀመጠ፤ ከሰማይም እንዲህ የሚል ቃል መጣ፤ “ይህ የምወደው በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ነው፤ እርሱንም ስሙት።”

በዚች ዕለት ጌታችን ራሱን ገልጦአልና ከዚህ በፊት ሠላሳ ዓመት ያህል ራሱን አልገለጠም ነበር፤ ግን በዚች ዕለት ለእስራኤል ልጆች ራሱን ገለጠ፤ “እነሆ የእግዚአብሔር በግ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ” ብሎ መጥምቁ ዮሐንስ እንደገለጠው የከበረ ወንጌል ምስክር ሆነ።

“እኔ አላውቀውም ነበር፤ ነገር ግን እስራኤል ያውቁት ዘንድ በውኃ ላጠምቅ ስለዚህ መጣሁ” አለ። በዚህም በዓል የእግዚአብሔር ልጅ የክርስቶስ የጌትነቱ ክብር ተገልጧል፤ እርሱም የዓለሙን ሁሉ ኃጢአት ለማስወገድ የሚሰዋ የእግዚአብሔር አማናዊ በግ ነው።

ስለዚህም ይህ በዓል በክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ዘንድ የከበረና ከፍ ከፍ ያለ ሆነ በርሱም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥምቀቱ በአከበረው ውኃ ይነጹበታል፤ የተቀበሉትንም ንጽሕና ጠብቀው ቢኖሩ በውስጡ የኃጢአታቸውን ሥርየት ያገኛሉ።

ስለዚህም ከክፉ ነገር ሁሉ ተጠብቀን የፈጣሪያችንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን የቸርነቱን ብዛት ልናመሰግን ይገባናል፤ እርሱ ስለ እኛ ሰው ሆኖ ከኃጢአታችን አድኖናልና።

ለእርሱም ከቸር አባቱ ሕይወት ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ክብር ምስጋና ስግደትም ይሁን፤ ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን!!!

መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ጥር፣ ፲፩

 

ለፈጣሪ በበጎ ፈቃድ መገዛት ይገባል!

ጥር ፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ሰው በራሱ ፈቃድ በጎ አልያም በክፉ ሐሳብና ምኞት መጥፎ ሊሆን ይችላል፡፡ የአዳም ዘር ጥንተ ተፈጥሮውን ዐውቆና ተረድቶ በድንቅ ሥራው ለፈጠረው አምላክ ተገዢ የመሆን ፈቃድም የራሱ ነው፡፡ በውዴታ ብቻ ሳይሆን በግዴታም ለፈጣሪ መገዛት እንዳለብን ቅዱሱ መጽሐፍ ያስተምረናል፡፡

ታዲያ ዓለምን ሁሉ ከእነ ጓዟ ለፈጠረ አልፋና ዖሜጋ፣ ኤልሻዳይ ለሆነው እግዚአብሔር መገዛት በፍቅር መሆን ሲገባው ብዙኃኑ ሰው ግን አሻፈረኝ ብሏል፡፡ ይባስ ብሎም በራሱ ፈቃድ ያለ እግዚአብሔር አምልኮ ለመኖር መወሰኑ ሳያንስ ዓለምን መግዛት እንደሚቻለው እያሰበ ነው፡፡ ሰው በራሱ ጥበብ ተጉዞ ጨረቃን አልያም ሌሎች በሰማያት ላይ ያሉ ድንቅ ፍጥረታት ላይ መድረስ ቢችልም ወደ ላይ የመምጠቅ ኃይሉ የተገደበ እንደሆነ ግን ማመን አዳግቶታል፡፡ ምንም መሣሪያ ቢሠራ፣ ምንም ተጠብቦ ወደ ሰማይ መጓዝ ቢችል እርሱ ባወቀ እንጂ የትም መድረስ አንችልም፡፡ ‹‹እንደ ንስር መጥቀህ ብትወጣ፣ ቤትህም በከዋክብት መካከል ቢሆን አወርድሃለሁ›› ተብሎ እንደተጻፈ (አብድ. ፩፥፬) ጥበብም ከእግዚአብሔር በመሆኑ እርሱን ባለመፍራት የሚደረግ ነገር ማንም ምንም ማድረግ አይቻለውም፡፡

አጋእዝተ ዓለም ሥላሴ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ ዛሬም ያለ ወደ ፊትም ዓለምን አሳልፎ የሚኖር ዘለዓለማዊ አምላክ የሆነ ማንም ሊያሸንፈውም የማይችል ነው፡፡ በቸርነቱ ብዛት ዓለምን ሲፈጥርም መልካም በመሆኑ ነው፡፡ ሰው ግን አምላክነትን ሽቶ ክሕደት ፈጸመ፤ ኃጢአት ሠራ፤ ከክብሩም ተዋርዶ መከራና ሥቃይ፣ ረኀብ፣ ጥም፣ እንግልት፣ ልፋት፣ ገዓር፣ ኀሣር ወዳለባት ምድር ተጣለ፡፡ በዚህም ሆኖ ሰው አምላኩን መበደል አላቆመም፡፡ የተፈቀደለትን ትቶ ያልተቀደለትን፣ የታዘዘውን ሳይፈጽም ያልታዘዘውን፣ የማይገባውን በመሻትም ፈጣሪውን መዳፈር ቀጠለ፡፡ ኃጢአት መሥራቱ ሳያንስ አምላክ ላይ መድረስ፣ ወደ ላይ መጥቆ ፈጣሪን ተዳፈረ፡፡

በኖኅ ዘመን የተፈጸመው የባቢሎናውያን ድርጊትም የዚህ ማሳያ ነው፡፡ በክፉ ምክራቸው ተነሣሥተው ፈጣሪ ወዳለበት ለመድረስ የሰናዖር ግንብን ሠሩ፡፡ መጽሐፉም እንደሚነግረን  ‹‹እግዚአብሔርም የአዳም ልጆች የሠሩትን ከተማና ግንብ ለማየት ወረደ። እግዚአብሔርም አለ። ‹‹ኑ፥ እንውረድ፤ አንዱ የአንዱን ነገር እንዳይሰማው ቋንቋቸውን በዚያ እንደባልቀው።›› (ዘፍ.፲፩፥፩-፱)

ታሪኩን በመቀጠል ስናነበውም አጋእዝተ ዓለም ሥላሴ የሰናዖርን ግንብ አፍርሶ ባቢሎናውያኑን በትኗቸዋል፡፡ የቅድስት ሥላሴ አንድነታቸውና ሦስትነታቸው የተገለጸበት ጥር ሰባት ቀን የከበረ በዓል እንደመሆኑ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡

ዓለማችን በጎርፍ እየተጥለቀለቀች፣ በመሬት መንቀጥቀጥ እየራደች፣ በሰደድ እሳት እየተለበለበች ያለችው የአዳም ዘር አምላኩን ክዶ፣ ሀብት፣ ሥልጣንና ኃይል በመሻት በኃጢአት ሰንሰለት ታስሮ የጠላት ዲያብሎስ ተገዢ በመሆኑ ነው፡፡ ወደ ላይ እየመጠቅን ሲመለስን ወደ ታች እየወረድን እንደሆነ ማን በነገረን? በሰው ሠራሽ ሥሪት የሚንቀሳቀሱ  ቁሳዊ አካላትን በመሥራት የአምላክን ክቡር ፍጡር ሰውን ለመተካትና ፈጣሪ ለመሆን፣ ከዚያም ባሻገር የተፈጥሮ ሂደትን በሚያዛባ መልኩ ዘር የመተካትን ሂደት ሰው ሠራሽ የማድረግ ጥረት አምላክነትን የመሻት ነው፡፡ ይህም የዳረገን ለከፋ ነገር መሆኑ በግልጽ የሚታይ ሆኗል፡፡ እኛ የማይገባንን ለማግኘት ስንጥር የሚገባንን ግን ተነጠቅን፡፡ ሰው የመሆን መብታችንን አጥተናል፡፡ በነጻ፣ ያለ ክፍያ ድንቅ ተደርገን ተሠርተን እኛ ግን በውድ ዋጋ ቁሳዊ አካልን ሸምተን የሰውን ሥራ ሁሉ እንዲሠራልን ተመኘን፡፡ የራሳችንን ክብር የሚያሳጣን ነገር መሆኑን ግን ለማወቅ ዓይነ ልቡናችን ታወረ፡፡

ጥበበኛ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር በሕገ ልቡና፣ በሕገ ኦሪትም ሆነ በሕገ ወንጌል የገለጠልን ምሥጠር ድንቅ ሥራውን ብቻ ሳይሆን በክብር ዘለዓለማዊ ሕይወትን የሚያሰጥ ነው፡፡ ከሁሉም አስቀድሞ ግን እርሱን መፍራት ያስፈልጋል፡፡ ‹‹የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው›› እንዲል፡፡ (ምሳሌ ፩፥፯) ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ ክብሩን አላወቀም፡፡ ስለዚህ የጥንተ ተፈጥሮአችንን አስታውሰን፣ የተፈጠርንበትን ምክንያትን ዐውቀንና ተድረተን፣ ለአምላካችን ለእግዚአብሔር በበጎ ፈቃድ በመገዛት ልንኖር ይገባል፡፡

አምላካችን ቸርነቱንና ምሕረቱን ያብዛልን፤ ከበዓሉ ረድኤትና በረከት ያሳትፈን፤ አሜን!

 

 

በዓለ ግዝረት

ጥር ፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

በዘመነ ብሉይ ግዝረት የተጀመረው በአባታችን አብርሃም ነበር፤ በዚያን ጊዜ የነበሩ ሕዘበ እግዚአብሔር ከአሕዛብ የሚለዩበትና ክብር የሚያገኙበት ሕግ መጽሐፊያዊ ግዝረት ነበር፡፡ ያም እንደ ጥምቀት ይሆንላቸው ነበርና ነው፡፡ (ዘሌ.፲፪፥፫)

የከበረ ወንጌል እንደገለጸው በዘመነ ሐዲስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በስምንተኛው ቀን ግዝረትን ፈጽሟል፡፡ “ጌታ ሰው መሆኑ ሕገ ኦሪትን ሊሽር ባለመሆኑ ሥርዓተ ግዘረትን ፈጽሞልናል፡፡” (መዝገበ ታሪክ ገጽ ፻፵፩)

በቅዱስ ሉቃስ ወንጌል እንደተጻፈው “ሊገርዙት ስምንት ቀን በሞላ ጊዜ፥ በማኅፀን ሳይረገዝ በመልአኩ እንደ ተባለ፥ ስሙ ኢየሱስ ተብሎ ተጠራ። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ወደ ግዘረት ቤት ወሰደችው፤ ገራዡ ምላጩን ይዞ ቀረበ፤ ነገር ግን ምላጩ እጁ ላይ ሳላ ውኃ ሆኖ ፈሰሰ። ጌታችንም በተአምራት የተገረዘ ሆኖ ተገኘ፡፡”  (ሉቃ.፪፥፳፩-፳፫)

የአምላካችን ድንቅ ሥራ ተነግሮ አያልቅምና በከበረች በጥር ፮ ቀን ሥርዓተ ግዝረትን የፈጸመልን ጌታ እኛም እርሱን አብነት አድርገን ወንድ ልጆችን በስምንት ቀናቸው እንድናስገርዝ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህን ከጌታችን ዘጠኙ ንዑሳን በዓላት አንዱና የመጀመሪያው የሆነውን የተቀደሰ ቀን ታከብረዋለች፡፡

ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን፤ አሜን!

 

 

 

 

በበረት ውስጥ እነሆ ተወለደ!

በመዝሙርና ሥነ ጥበባት ክፍል

ታኅሣሥ ፳፰፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 

      ያቺ ድንግል ቤተ መቅደስ ሆና ሐርና ወርቅ ስታስማማ፣

መልአኩ የምትወልጅው ኢየሱስ ነው ያላትን ቃል ሳታቅማማ፣

የሚፈውስ ድውያንን፣

የሚያበራ ዕውራንን ፣

የሚተረትር ሽባዎችን ፣

የሚያነጻ ለምጻሞችን ፣

 የሚያወጣ አጋንንትን፣

ከስም በላይ ስም የሆነ፣

አልፋ ኦሜጋ የታመነ፣

ድንቅ መካር ሰው መሆንን የወደደ፣

በበረት ውስጥ እነሆ አሁን ተወለደ!

በአርያም የሚኖሩት መላእክቱ፣ ተመልክተው አምላክ ሲያዝን ለፍጥረቱ፣

ግርግም ከበው የዚያ ሕፃን ሠራዊቱ፣

በሰማያት አመስግነው እግዚአብሔርን

በምድር ላይ ለሰውም ልጅ ሰላም ይሁን

ብለው ዘምረው፣ ቤተ ልሔም የምድር ዙፋን፣

በአርያም ተሸክመው ቅዱስ አንተ የሚሉትን፣

ድንግል ማርያም ወዮሴፍ ላም አህያ ተመስለው አርባዕቱን፣

እነርሱ አንቺን ተሸክመው አንቺ ድገሞ ጸባኦትን

የአስተርእዮ ዘመን ሆኖ በምድር ላይ ሲከናወን

የሰማዩ ድንቅ ሥራ፣ ከበረት ውስጥ ሲፈነጥቅ ድህነት ፈውስን

ያነገበ የጽድቅ ጮራን፣

አንቺ ቅድስት ቤተ ልሔም፣

ቅጠል ለብሶ እንደ ሕፃን እያነባ መድኃኔ ዓለም፣

ኃያል ንጉሥ እርቃን ሆኖ ባንቺ ሲድር አልፈራሽም

እንደ ባሕር አልሸሸሽም

እንደ እምቦሳም አልዘለልሽም፡፡

እነ ኪሩብ በነደ እሳት የተሠሩ፣

በሁለት ክንፍ በዓለም ዙሪያ የሚበሩ፣

በመለኮት እሳትነት እንዳይጠፉ በሁለት ክንፍ ፊታቸውን የሠወሩ፣

በቀራቸው በሁለቱ እግራቸውን የጠፈሩ፣

 

  • ቅዱስ (፫)  ብለው ያለፋታ በመንቀጥቀጥ የሚያመልኩት፣

በግርግም ውስጥ እንደ ሕፃን ሲያለቅስ አይተው ምንስ አሉት

ፀሐይና ከዋክብትን ለፈጠረ፣

በልዩ ጌጥ ዓለማትን ላሳመረ፣

ነገሥተ ተርሴስ ወደሴያት፣

እጅ መንሻ አመሃውን ላመጡለት፣

ከዋክብትን በስማቸው ለሚጠራ፣

ፍጥረታትን ያለሳንካ ለሚሠራ፣

ከክብር አንሶ በራፊ ጨርቅ ተጠቅልሎ፣

አምላክ ሳለ ፍጡር መስሎ እንደ ነዳይ ተጎሳቁሎ፣

የዚያ ሌሊት ቢያይል ቁሩ፣

በደመ ነፍስ የሚኖሩ  ትንፋሽ ሰጥተው ሲገብሩ፣

መላእክቱ ቅዱስ(፫) ብለው በፍቅር ሆነው

የሚያመልኩት፣ በግርግም ውስጥ እንደ ሕፃን ሲያለቅስ አይተው

ምንስ አሉት ጽድቃችንም የመርገም ጨርቅ ከንቱ ሆኖ፣

መኖሪያችን በሲኦል ቋት ተወስኖ፣

ለዘመናት ስንገረፍ በእሳት ላንቃ፣

ያበቃ ዘንድ ይህ እንግልት ይህ ሰቆቃ፣

ልዑል ሁይ ክንድህን ስደድ፣

ናማ ውረድ

ና ተወለድ

ብለው ጻድቃን ሲጸልዩ ለዘመናት ፣

እርግማኑን ይሽረው ዘንድ በምርቃት፣

እነሆ አሁን

ጨለማውን አስወግዶ ብርሃኑን ያበራልን፣

ከጎሞራ ያልመሰለን ከሶዶም ግብር ያልደመረን፣

ሰማያትን በደመና የሚጋርድ፣

ተወለደ በዐውድ

እሰይ እሰይ ይኸው አሁን የምሥራች፣

የጸብ ግርዶሽ ተቀዳዶ ሰላም ሆኗል በላይ በታች፡፡

፶፻፭፻ የንስሐ የጣር ዘመን ተፈጸመ

አምላክ ወሰብእ በግርግም ውስጥ ከበጎች ጋር ከተመ!

 

 

 

የሃይማኖት ተክል!

ታኅሣሥ ፳፫፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ድንቅ በሆነው የፈጣሪ ሥራ ሰው ሆነን ተፈጥረን በዚህ ዓለም ላይ ስንኖር የሕይወታችን መሠረት በሆነው ሃይማኖት ጸንተንና በቀናው መንገድ ተጉዘን የመንፈስ ፍሬን ለማፍራት እንዲቻለን ነው፡፡ የማንኛውም መንፈሳዊነት መሠረት ሃይማኖት ነውና፡፡ አንድ አምላክን ማመን ለእርሱ መታመን ሃይማኖት ነውና፤ ይህ ምሥጢር ገብቷቸው፣ በድንቅ ሥራቸው አብርተው፣ ፍጹም ተጋድሎአቸውን ጨርሰው ለአምላካቸው እውነተኛ ምስክሮች በመሆን ርስተ መንግሥተ ሰማያትን የወረሱ ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን የቤተ ክርስቲያናችን ዕንቁ ፈርጥ በመሆናቸው እናከብራቸዋለን፡፡

“የሃይማኖት ተክል” የተባለው ቅዱስ አባታችን ኢትዮጵያዊው ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የከበረች ልደት በዓሉ በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ይከበራል፡፡ ጻድቁ በብሥራተ ቅዱስ ሚካኤል መሠረትም በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ልዩ ስሙ ኢቲሳ በሚባል ቦታ መጋቢት ፳፬ ተፀንሰው ታኅሣሥ ፳፬ የተወለዱት ከአባታቸው ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው እግዚ ኅረያ ነው፡፡

በተለወዱ በሦስተኛው ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ     ወርደው    ‹‹ሐዱ  አብ  ቅዱስ፤   አሐዱ  ወልድ  ቅዱስ፤  አሐዱ  ውእቱ  መንፈስ  ቅዱስ፤  አንዱ  አብ  ቅዱስ  ነው፤  አንዱ  ወልድ  ቅዱስ  ነው፤  አንዱ  መንፈስ  ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት አጋእዝተ ዓለም ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ ወላጆቻቸው ያወጡላቸው ስም ‹‹ፍሥሐ ጽዮን››  የሚል ቢሆንም‹‹ተክለሃይማኖት›› ደግሞ ጌታችን እራሱ ነው፡፡

የሃይማኖት ተክል የተባሉት ቅዱስ አባታችን የወንጌልን ቀንበርን ተሸክመው፣ ሀገራችን ኢትየጵያን በዕርፈ መስቀል ያረሱ፣ ቅዱስ ቃሉን ሰብከውና አስተምረው፣ እውነተኛ ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ሃይማኖትን ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን ለዓለም አሳውቀው፣ ጣዖታትን ሰባብረው ቀጥቅጠው ያጠፉ፣ ብዙዎችን ከኃጢአት ጎዳና መልሰው ለርስተ መንግሥተ ሰማያት ያበቁ ታላቅ አባት ናቸው፡፡

የአባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ጸሎት፣ አማላጅነትና ረድኤት አይለየን፤ አሜን!!!

ምንጭ፡ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት

 

‹‹እነርሱ በእምነት የእሳት ኀይልን አጠፉ›› (ዕብራውያን ፲፩፥፩)

ታኅሣሥ ፲፯፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ለብዙዎቻችን እሳትን የሚያጠፋው ውኃ ብቻ ይመስለናል፡፡ ለእግዚአብሔር የታመኑ ቅዱሳን ሰማዕታት የእሳትን ኃይል በትዕግሥታቸው እንዳጠፉትና ጸሎታቸውም ለእኛ በአማላጅነታቸው ለምንታመን ምእመናን ሁልጊዜም እንደሚያስፈልገን ፈልፈለ ማኅሌት የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ምስክር ሆኖ ያስተምረናል፤ አጥፍኡ ኃይለ እሳት በትዕግሥቶሙ፤ ይብጽሐነ ወትረ ጸሎቶሙ፤በትዕግሥታቸው የእሳትን ኃይል አጠፉ፤ ጸሎታቸው ዘወትር ይድረሰን” እንዲል፤ (ድጓ ዘታኅሣሥ ፪)

በሐዲስ ኪዳን ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እምነት ማለት ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የምታረጋግጥ ፣ የማናየውንም ነገር የምታስረዳ ናት››  በማለት የተናገረውን ቃል (ዕብራውያን ፲፩፥፩) በብሉይ ኪዳን አስቀድሞ በተፈፀመ ገድል እንድናውቀው የሠለስቱ ደቂቅ የባቢሎን የዱራ ሜዳ ገድልና የእምነት ጽናት ዓይነተኛ የሕይወት ትምህርት እንዲሆነን በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፎልን እናገኛዋለን፡፡ እምነታችን እውነተኛ ሆኖ የሚገለጠው እግዚአብሔር በሚፈጽምልን የትድግና ሥራ ብቻ ሳይሆን መከራም ቢመጣ የመጣው እግዚአብሔር ፈቅዶ በመከራው ተፈትነን ካለፍን በኋላ እኛ ልጆቹ እንድናገኝ የፈለገውን ሰማያዊ አክሊልና ዋጋ እንድናገኝም ስለሚፈልግ መሆኑን ማመን ስንችል ነው፡፡

ጻድቁ አባታችን ቅዱስ ኢዮብ  እጅግ ብዙ መከራ ሲደርስበት ‹‹ከእግዚአብሔር እጅ መልካሙን ተቀበልን፤ ክፉውን ነገርስ አንታገሥምን?›› በማለት በደረሰበት ነገር ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት በከንፈሩ ሳይበድል የሕይወቱን የፈተና ጊዜ ለማሳለፍ በቅቷል፡፡ (መጽሐፈ ኢዮብ ፪፥፲) የሠለስቱ ደቂቅ እውነተኛ እምነትም ለናቡከደነፆር በሰጡት ምላሽ ውስጥ የምናገኘው ነው፡፡ ንጉሥ ናቡከደነፆርም እኔ ላሠራሁት ምስል ስገዱ ባላቸው ጊዜ  ‹‹ናቡከደነፆር ሆይ! በዚህ ነገር እንመልስልህ ዘንድ አንፈልግም፡፡ ንጉሥ ሆይ! እኛ የምናመልከው አምላክ በሰማይ አለ፤  ከሚነድደው ከእሳቱ እቶን ያድነን ዘንድ ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል፤ ንጉሥ ሆይ! ይህም ባይሆን ፣ አማልክትህን እንዳናመልክ ፣ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንዳንሰግድለት ዕወቅ›› አሉት፡፡ (ትንቢተ ዳንኤል ፫፥፲፭-፲፰)

ከዚህ በኋላ ወደ እሳት እንዲጨመሩ ንጉሡ አዘዘ፡፡ አይደለም እሳት ላይ ተጥደን በመልካም ሁኔታ ውስጥ ሆነን እንኳን የእግዚአብሔርን ስም መጥራት ላቃተን ለእኛ፣ ሠለስቱ ደቂቅ በእሳት መካከል ሆነው የእግዚአብሔርን ስም መጥራት ብቻ ሳይሆን ረጅም ጸሎትን ሲያደርሱ

 

እንደነበር ማወቅ ምንኛ ግሩም ነው! (ወጸለዩ ማዕከለ እቶነ እሳት ነዋኃ ጸሎተ) (መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ታኅሣሥ ፪)፡፡

በመከራ ላይ መከራ ቢያጸኑባቸው በምስጋና ላይ ምስጋና በመጨመር ታላቅ የሆነ የነገረ ክርስቶስ ትምህርትንም የያዘ ጸሎት ያደረሱት በእሳት ውስጥ ነው ቢባል ማን ያምናል፡፡ በጸሎታቸው እነርሱ ይህን ገድል ከፈፀሙ ከ፮፻ ዓመት በኋላ አምላክ የሰውን ሥጋ ለብሶ ተገልጦ እንደሚወለድ እና በዚህች ምድርም ፴፫ ዓመት እንደሚቆይ የሚያጠይቅ ነው፡፡

ሰው እግዚአብሔርን ካመነና ማመኑንም በሥራ ገልጦ ካከናወነ ፍጹም የሆነ የእግዚአብሔር ረድኤት ከእርሱ ጋር ስለሚሆን በሥጋ ዓይን ስናየው በሥጋው ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርስበት የሚችል እሳት እንኳን አቅም ያጣል፡፡ ሠለስቱ ደቂቅን ወደ እሳት ወርውረው እንዲጨምሩ በንጉሡ የታዘዙትን ሰዎች የገደለ እሳት በመካከሉ የተገኙ ሠለስቱ ደቂቅ ላይ ግን አንዳች ጉዳት ማድረስ አልቻለም፡፡ የራሳቸው ጠጉር አንዲት ዘላላ እንኳ አልተቃጠለችም፤  ሰናፊላቸውም አልተለወጠም፤ ሽታቸውንም አልለወጠም፡፡ (ትንቢተ ዳንኤል ፫፥፳፯)

ጥንተ ጠላት ዲያቢሎስ በዓላውያን ነገሥታት ላይ አድሮ ዛሬም በእኛ ላይ የጥላቻን እሳት እያነደደ ከራሳችን አልፎ ለሀገራችን ኢትዮጵያም የሚተርፍ መከራን አኑሯል፡፡ የባቢሎንን እሳት በመስቀሉ በማቀዝቀዝ ሠለስቱ ደቂቅን ከእግዚአብሔር ተልኮ ያዳነው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በእኛና በሀገራችን ኢትዮጵያ እየነደደ እጅግ መከራ ውስጥ የከተተንን የጥላቻ እሳት እንዲያበርድልንና ሁላችንም የፍቅር ሰው እንድንሆን አማላጅነቱና ጠብቆቱ አይለየን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

 

በአታ ለእግዝእትነ ውስተ ቤተ መቅደስ

ከደጋጎቹ ቅዱሳን አባቷና እናቷ ኢያቄምና ሐና የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ቀን የከበረ ነው፡፡ በበጎ ምክር በእግዚአብሐርም ፈቃድ ይህ ሆነ፤ በዚያን ጊዜ ኢያቄምና ሐና “….ሆዷ ዘመድ ሳይወድ አፏ እህል ሳይለምድ ወስደን እንስጥ” ብለው በመማከር መባዕም ጨምረው ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ፡፡   

ተዝካረ ልደቱ ለኤልያስ ነቢይ

ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ቅዱሳት መጻሕፍት ነቢዩ ኤልያስ የተወለደው በታኅሣሥ ፩ ቀን ከነገደ ሌዊ እንደሆነ ይገልጻሉ፤ የአባቱ ስም ኢያስንዩ የእናቱ ስም ቶና ይባላሉ፡፡ በተቀደሰች የልደት ቀኑም አባቱ ብርሃን የለበሱ አራት ሰዎች ሲሰግዱለትና ሕፃናት በሚጠቀልሉበት ጨርቅ ፈንታ በእሳት ሲጠቅልሉት  ተመልክቷል፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ዘኅዳር ፩፣ መዝገበ ታሪክ ገጽ ፹፬)

ኢትዮጵያ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተአምኆ ቅዱሳን መጽሐፉ ስለዚሁ ነቢይ እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ “ቴስቢያዊ (የቴስቢያ ሰው)፤ ኮሬባዊ (ወደ ኮሬብ ተራራ የወጣ)፣ ታቦራዊ (በታቦር ተራራ የተገኘ)፣ ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን የለጐመ ለሆነ፣ የጸሎቱ ቃልም በአዶናይ ዦሮ ውስጥ ለተሰማ፣ ውኃውን እስኪበላ ደርሶ እሳትን ከሰማይ ያወረደ ለሆነ፣ በእሳት ሠረገላ ተጭኖ ወደ ተድላ ደስታ ቦታ ለገባ ለነቢዩ ለኤልያስ ሰላምታ ይገባል።”

ሊቁ አርከ ሥሉስም በአርኬ መጽሐፉ ላይ ደግሞ እንዲህ ብሏል፤ “ምድራዊ የሆነ የዓለም ሕይወትን አራግፈህ ለማረፍ ወደ ሰማያት ያረግህ ለሆንክ ለአንተ ለኤልያስ ሰላም እላለሁ፡፡ አክአብን ለተናቀ ሥራው እየዘለፍከው ጣዖታትን የቀጠቀጥክ ማምለኪያዎቹን ያፈረስክ በምስጋናህ ምንኛ ተመሰገንህ።”

ቅዱሱ መጽሐፍ የዚህን ፈፍ  ነቢይ ስም “ኤልያስ” ፻ (መቶ) ጊዜ ጠቅሶታል፡፡ ድንቃ ድንቅ ተአምራቱንም መዝቦት እናገኛለን፤ ከእነዚህም መካከል አክአብና ኤልዛቤል ጣዖት በማምለከታቸው ኤልያስ ሦስት ዓመት ከ ስድስት ወር ዝናብን በጸሎቱ አቁሟል፡፡ (፩ኛ ነገ. ፲፯)፤ የሰራጵታዋን መበለት የሞተ ልጇን አስነሥቷል፡፡ (፩ኛ ነገ.፲፯፥፲፱)

ለአምላካችን እግዚአብሔር ያቀረበውን መሥዋዕት እሳት ከሰማይ ወርዶ የበላለት ነቢይ እንደሆነም መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፤ (፩ኛ ነገ ፲፰) ከሦስት ዓመት ከስድስት ወር በኋላ ቀርሜሎስ ወጥቶ በመጸለይ ዝናብ እንዲዘንብ አድርጓል፤ (፩ኛ ነገ. ፲፰) አካዝያስ የላካቸውን ፶ (ኀምሳ) አለቃዎች እሳት ከሰማይ አውርዶ አቃጥሏል፤ (፪ኛ ነገ. ፩) በመጐናጸፊያው የዮርዳኖስን ወንዝ ከፍሏል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፬) በእሳት ሠረገላ በዐውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጥቷል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፩)፣ በደብረ ታቦር ጌታ ምሥጢረ መንግሥቱን ሲገልጽ ከሙሴ ጋር ዐብሮ ተገኝቷል፤ (ማቴ.፲፯፥፬) ዳግመኛ በመምጣት በሐሳዌ መሲሕ ጊዜ ሰማዕትነትን ይቀበላል፡፡ (ማቴ.፲፯፥፲፩)

የነቢዩ ኤልያስ በረከት ይደርብን!