5ኛው ሀገር አቀፍ ዓመታዊ ዐውደ ጥናት ተካሔደ
መስከረም 3 ቀን 2006 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል የተዘጋጀው 5ኛው ሀገረ አቀፍ ዓመታዊ ዐውደ ጥናት “ጥናትና ምርምር ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተልዕኮ መጠናከር” በሚል ጳጉሜ 2 እና 3 ቀን 2005 ዓ.ም. በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አዳራሽ ተካሄደ፡፡
በመክፈቻ መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት መልእክት “እግዚአብሔር ሲፈቅድ ልጆቹን ለመልካም ነገር ያውላቸዋል፡፡ የዚህ ጉባኤ ዓላማም ለመልካም ሥራ ነው፡፡ መልካም ሰዎች ለመልካም ነገር ይውላሉና፡፡ ሰው ሰውን አፍቃሪ፤ ረጂ፤ ለሀገሩም ለእግዚአብሔር የተመቸ እንዲሆን ያደርጋል፡፡ የዘመኑ የፈጠራ ትምህርት ከመንፈሳዊ ትምህርት ጋር በተያያዘ መመራመርን ይጠይቃል፡፡ ሰው ካወቀ ለሌላው ያሳውቃል፤ ለሌላው ያስረዳል፤ መልካም መሳሪያም ይሆናል፡፡ ይህ የተጀመረው ምርምርና ጥናት እኛንም የበለጠ ያፋቅረናል፤ በሃይማኖት እንድንቆም፤ የበለጠም እንድንሠራ ያደርገናል፡፡ የተሸሸገውን ታሪካችንን፤ያሳውቀናል፤ ልጆቻችንንም ተረካቢ ያደርጋቸዋል፡፡ ጥሩ ጅምር በመሆኑ በዚሁ እንድንቀጥል ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡