ጥምቀት

በዘመነ ሥጋዌ በናዝሬት ከተማ፤ ዮርዳኖስ ወንዝ የእስራኤል ሕዝብ በመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ተራ ይዘው በሚጠብቁበት ጊዜ እርሱ እንዲህ እያለ ይሰብክ ነበር፤ ‹‹እናንተ የእፉኝት ልጆች፥ ከሚመጣው መቅሠፍት ታመልጡ ዘንድ ማን ነገራችሁ? እንግዲህ ለንስሓ የሚያበቃችሁን ሥራ ሥሩ፤ አብርሃም አባታችን አለን በማለት የምታመልጡ አይምሰላችሁ፤ እግዚአብሔር ከእነዚህ ድንጋዮች የአብርሃም ልጆችን ማንሣት እንደሚችል እነግራችኋለሁ፡፡ እነሆ፥ ምሳር በዛፎች ላይ ተቃጥቶአል፤ መልካም ፍሬ የማያፈራውን ዛፍ ሁሉ ይቈርጡታል፤ ወደ እሳትም ይጥሉታል፡፡›› (ሉቃ.፫፥፯-፱)

ሕዝቡም ምን ቢያደርጉ እንደሚሻል በተራ በተራ ይጠይቁት ጀመር፤ እርሱም ለእያንዳንዱ ሲመልስ፤ ሁለት ልብስ ያለው አንዱን ለሌለው እንዲሰጥ፣ ለተራበ እንዲያበላ፣ ቀራጮችን ደግሞ ከታዘዙት አትርፈው አንዳይውስዱ እንዲሁም ጭፍሮችን በማንም ላይ ግፍ እንዳይፈጽሙ እየመከረ አጠመቃቸው፡፡ እነርሱም በልባቸው እጅግ እያደነቁ ከጌታችን ኢየሱስ ጋር መሰሉት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን እንዲህ አላቸው ‹‹እኔ በውኃ አጠምቃችኋለሁ፤ ግን የሚበልጠኝ የጫማውን ማሰሪያ እንኳን ልፈታለት የማይገባኝ ይመጣል፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ፣ በእሳትም ያጠምቃችኋል፡፡›› (ሉቃ.፫፥፲፮-፲፯)

ሕዝቡ ሁሉም ከተጠመቁ በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ውስጥ ገብቶ ሊጠመቅ ወደ እርሱ ሲጠጋ ቅዱስ ዮሐንስ ግን ‹‹እኔ በአንተ ልጠመቅ እሻለሁ፤ አንተ ወደ እኔ ትመጣለህን?›› በማለት ከለከለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ አሁንስ ተው፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናልና›› አለው፡፡ እርሱም ተወው፤ ጌታችን ኢየሱስም ከተጠመቀ በኋላ ወዲያውኑ ከውኃ ወጣ፤ በዚይች ቅጽበትም ሰማይም ተከፈተ፤ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ ሲቀመጥ አየ፡፡ እነሆም በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወድደው ልጄ ይህ ነው የሚል ድምጽ ከሰማይ መጣ፡፡›› (ማቴ.፫፥፲፫-፲፯)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ ልጁ መሆኑን እግዚአብሔር አብ ልጄ ብሎ መሰከረ፤ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ወረደ፤ ወልደ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ ተጠምቆ በፅንፈ ዮርዳኖስ ታየ፡፡
እግዚአብሔር አምላክም ለአዳም የገባለነትን ቃል ለመፈጸም አንድ ልጁን ልኮ ከኃጢአት ባርነት አወጣው፡፡ ስለዚህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣው አዳምን እና ሔዋንን ከባርነት ነፃ ለማውጣትና ድኅነት ሊሆናቸው ነውና በጥምቀቱ ጊዜ በዮርዳኖስ ወንዝ በሰይጣን ተቀብሮ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤያቸውን ቀደደላቸው። ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ በማለት ተናግሮታል። ‹‹እናንተም በበደላችሁና ሥጋችሁን ባለመገረዝ ሙታን በሆናችሁ ጊዜ፥ ከእርሱ ጋር ሕይወትን ሰጣችሁ። በደላችሁን ሁሉ ይቅር አላችሁ። በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰ፤…።›› (ቆላ.፪፥፲፫-፲፬)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለነፍሳችን ድኅነት ይሆነን ዘንድ ተጠምቆ አርአያ ሆኖናል፡፡ በጥምቀቱም ጥምቀትን ባርኮልናል፤ በኦሪት ጥምቀት ሥጋን እንጂ ነፍስን አይፈውስምና እርሱ በተጠመቀው ጥምቀታችን ተባረከልን፡፡
እኛም ስንጠመቅ በአዳም በደል ተወስዳ የነበረች ልጅነታችን ተመልሶ፣ የዕዳ ደብዳቤያችንም እንዲደመሰስልን አስረዳን፡፡ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም ቀደማዊና ደኃራዊ እንደሌለው እንደተመሰከረ እኛም ስንጠመቅ ከሥላሴ መወለዳችን ይረጋገጥልና፡፡ (ዮሐ. ፫፥፭፣ የሐዋ. ፪፥፴፰፣ ቆላ. ፪፥፲፩-፲፬)

ጥምቀት ለክርስቲያኖች ሁለተኛ ልደታቸው ነው፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሁሉ ወደ ፈቃደ ሥጋው ስለሚያደላ መንፈሳዊ ልደት ያስፈልገዋል፡፡ ‹‹ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር ወደ የእግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡›› (ዮሐ. ፫፥፫-፭)
በዘመነ ብሉይ ይፈጸም የነበረው ጥምቀት የንስሓ ጥምቀት ነበር፡፡ በሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ንስሓ ግቡ ኃጢአታችሁ ይሠረይ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ›› ብሏቸው እንደተናገረው ጥምቀት ኃጢአትን ያስተርይልናል፡፡ (ሐዋ. ፪፥፴፯-፴፰)
በሐዲስ ኪዳን የሚፈጸመው ግን የልጅነት ጥምቀት ነው፤ ይህን ተከትሎ ወንድ ልጅ በዐርባ ሴት ልጅ በሰማንያ ቀን ይጠመቃሉ፡፡ የዚህም ምክንያት አዳም በተፈጠረ በ፵ ቀኑ፣ ሔዋንም በተፈጠረች በ፹ ቀኗ ወደ ርስታቸው ገነት እንደገቡ ሕፃናትም በ፵ እና በ፹ ቀናቸው ተጠምቀው የሰማያዊት ኢየሩሳሌም አምሳል ወደሆነችው ወደ ቤተ ክርስቲያን ይገባሉ፡፡
በተጨማሪም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ነገር ግን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እኛ ሁላችን በሞቱ እንደተጠመቅን ሁላችሁ ይህን ዕወቁ፤ እኛ ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደ ተጠመቅን አታውቁምን? እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደተነሣ እንዲሁ እኛ በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን›› በማለት በጥምቀት ክርስቶስን እንደምንመስለው ተናግሯል፡፡ ‹‹ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን›› የሚለውን በገቢር ለመግለጽ እንዲሁም ‹‹በጥምቀት ደግሞ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር ሥራ በማመናችሁ ከእርሱ ጋር ተነሳችሁ›› ያለውን እንዲሁ በድርጊት ለማሳየት ነው፡፡ (ሮሜ ፮፥፫-፬፣ቆላ. ፪፥፲፪)

‹‹ያመነ የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ ያልተጠመቀ ይፈረድበታል›› እንደተባለው ከገሃነመ እሳት ፍርድ እንድናለን። ሰው ክርስቲያን ይባል ዘንድ ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ማግኘት አለበት፡፡ ይህም በልጅነት የሚያገኘው በረከት በተቀደሰ ውኃ በመጠመቁ ነው፡፡ ካልሆነ ግን የእርኩስ መፈንስ ማደሪያ ወይንም መናፈቅ ይሆናል ማለት ነው፡፡ (ማር. ፲፮ ፥ ፲፮)
በእምነት ለተጠመቀ ሰው ግን ጥምቀት ፈውሰ ሥጋን እንዲሁም ፈውሰ ነፍስን ይሰጣል፤ ምክንያቱም እምነት ኃይልን ታደርጋለችና ጥምቀት ድኅነት መሆኑን አምነን ከተጠመቅን ኃጢአታችን ይሠረይልናል፤ ይህም ጌታችን ጥምቀትን ባርኮ ስለሰጠን በምሥጢረ ጥምቀት የምንረዳው ነው፡፡

ጌታችን ኢየሱስ የጥምቀትን ሥርዓት ከመሰረተልን በኋላ ደቀ መዛሙርቱን በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም የሰውን ዘር እንዲያጠምቁ አዟቸዋል፡፡ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ተከታዮች በሙሉም በምሥጢረ ጥምቀት እንደምንረዳው ሥርዓቱን ጠብቀን እንጠመቃለን፤ ይህም ሥርዓት ከዋዜማው ከተራ ጀምሮ የሚፈጸም ነው፡፡ (ማቴ. ፳፰፥፲፱-፳)
የጥምቀት በዓል በእነዚህ ሁለት ቀናት ውስጥ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን በዓለ ጥምቀት እና ተግባር የሚያመለክቱ ብዙ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓቶች ይከናወናሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጠፋውን ፍጥረቱን ፍለጋ ወደ ዓለም እንዴት እንደወረደ የሚገልጹ ያሬዳዊ ዝማሬዎች እና መዝሙሮች በከተራ ይዘመራሉ፡፡

ሁሉም የቃል ኪዳኖች (ታቦቶች) በእያንዳንዱ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በአቅራቢያው ውኃ ወዳለበት ወደ ጅረት ገንዳ ይሄዳሉ፡፡ የዚህም ምሥጢር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከኢየሩሳሌም ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ እንዴት እንደሄደ የሚያሳይ ነው፤ አንድ ሌሊት ማሳለፉ ጌታችን በትህትና የእርሱን ተራ መጠበቁን የሚያሳይ ነው፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ እጅ ከተጠመቁት ሕዝቦች መካከል ተጠምቋልና፡፡ ይልቁንም ተራውን በመጠበቅ የትህትናን ተግባር አሳይቶናል፡፡ ታቦታቱም ከሕፃናት፣ ከወላጆች፣ ከወጣቶች፣ ከአረጋዊያን፣ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች፣ ከቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት እና ከሌሎችም ምእመናን ጋር በሁሉም ክርስቲያኖች ይታጀባሉ፡፡

ሌሊቱን በውዳሴ በማኅሌት ካሳለፉ በኋላ ውኃው በፓትርያኩ፣ በሊቀ ጳጳሳት እና በካህናት ከመባረኩ በፊት ማለዳ ቅዳሴ ይጀምራል፤ ምእመናንም የቅዳሴ አካል ለመሆን ቀደም ብለው ይገኛሉ፡፡ ሃይማኖት አባቶችም ውኃውን በአብ፣ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ከባረኩት በኋላ ወደ ተሰበሰቡት ክርስቲያኖች በብዛት ውኃውን ለመርጨት ዝግጅት ያደርጋሉ፡፡

በዚያን ጊዜ ክርስቲያኖች በሺዎች ከሚቆጠሩ ዓመታት በፊት በዓይነ ኅሊናቸው ወደኋላ በመመለስ የጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀት በማሰብ ከተረጩ በኋላ በደስታ ታቦታቱን በኅብረት ወደየቤተ ክርስቲያን በማጀብ ይጓዛሉ፤ ካህናቱም የያሬድን ዝመሬ በመዘመር በዓሉን ያከብራሉ፡፡

ሕፃናት፣ ወጣቶች እንዲሁም አረጋዊያን በሙሉ በዝማሬው ይሳተፋሉ። የቅዱሱ ታቦትም በደኅና ወደ መንበሩ ሲመለስ ሕዝቡ በመንፈሳዊ ደስታ ወደ ቤታቸው ይሄዳሉ፡፡ ኢትዮጵያውያን በዚህ አስደናቂ እና መንፈሳዊ ክርስቲያናዊ ምግባር አማካኝነት የእግዚአብሔርን ልጅ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ማወደሱን የቀጠልን ሲሆን ለመጪው ትውልድም ይህንኑ እንድናስተላልፍ በእምነት እና ሃይማኖት ልንጸና ይገባል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ በጥምቀቱ ፈውሰ ሥጋንና ፈውሰ ነፍስን ያድለን ዘንድ ፍቃዱ ይሁንልን፤ አሜን!

ልደተ ክርስቶስ

‹‹እነሆ ለእናንተና ለሕዝቡ ሁሉ ደስታ የሚሆን ታላቅ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤ እነሆ፥ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኅን ተወልዶላችኋል፡፡…››

የተስፋው ቃል

በአንዲት ፍሬ ቅጠል ሕይወትን አጥቼ
ርስቴን ተነጠኩ የሞት ሞትን ሙቼ
በግዞት ተነዳሁ በድቅድቅ ጨለማ
ወደ ፍዳ መንደር ወደ ሞት ከተማ…

ልደቱ ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት

ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር ሆኖ የሥላሴን መንበር ያጠነው ጻድቁ አባት አቡነ ተክለ ሃይማኖት የተወለዱበት ዕለት የተቀደሰች ናት፤ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ለአባታቸው ካህኑ ጸጋ ዘአብና ለእናታቸው ቅድስት እግዚእ ኀረያ ባበሠራቸው መሠረትም በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ልዩ ስሙ ኢቲሳ በሚባል ቦታ በታኅሣሥ ፳፬፤ ፲፪፻፲፪ ዓ.ም ተወለዱ፡፡ በሦስተኛው ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ አንዱ አብ ቅዱስ ነው፤ አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው፤ አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት ሥላሴን አመስግነዋል፡፡

‹‹ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ!›› (ማቴ.፯፥፲፭)

ነቢይ ማለት ተነበየ፣ ተናገረ ከሚለው የግእዝ ቃል የተወሰደ ሲሆን ትርጉሙም ወደፊት ስለሚሆነውና ስለሚመጣው አስቀድሞ መናገር፣ መተንበይ ማለት ነው፡፡ ከዚህም በተመሳሳይ ‹ናቪ› ከሚለው የዕብራይስጥ ቃል የተገኘ ስያሜ ነው፤ መምራት፣ ማብሠር፣ መምከር፣ መንገር የሚል ትርጓሜም አለው፡፡ ይህ ቃል ወደ ግሪክ ሲተረጎም ‹ፕሮፌቴስ› ወይንም ‹ፕሮ› እና ‹ፌሚ› ከሚሉት ጥምር-ቃላት የተገኘ በመሆኑ ‹ፕሮ› ቅድሚያ፣ ከአንድ ነገር በፊት ማለትን ሲያመለክት ‹ፌሚ› ደግሞ መናገር፣ ማብሠርና ማሳወቅ ማለት እንደሆነ መምህር ብዙነሽ ስለሺ ‹ትምህርተ ሃይማኖት› በተሰኘው መጽሐፋቸው ውስጥ ገልጸዋል፡፡ በዚህም መሠረት ‹ፕሮፌቴስ› የወደፊቱን ነገር አስቀድሞ መናገር፣ ማብሠር ወይም ማሳወቅ የሚል ትርጓሜ እንዳለው እንረዳለን፡፡ ምዕራባውያን በመጽሐፍ ቅዱሳቸው ውስጥ ቃሉን ‹ፕሮፌት› በሚለው ሲጠቀሙ የሴሜቲክ ቋንቋ ዘር የሆነው ግእዝ ከዕብራይስጡ ቃል ‹ናቪ› የሚቀራረብ ትርጓሜ በመውሰድ ነቢይ የሚለውን ቃል ይጠቀማል፡፡ (ትምህርተ ነቢያት ገጽ ፲፩)