አእመረ አሸብር “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ በቁጥጥር ሥር ዋለ

 

“የቅዳሴ ሥርዓት” እየፈጸምን ነው በማለት ሲያጭበረብሩ

                                                                                                                            በእንዳለ ደምስስ

 በጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘው አእመረ አሸብር ከግብረ አበሮቹ ጋር በግለሰብ ቤት ውስጥ “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በቁጥጥር ሥር ዋለ፡፡

 “መዳን በማንም የለም” በሚል ርእስ በ፳፻፲፩ ዓ.ም ባሳተመው የኑፋቄ መጽሐፉ በቅዱስ ሲኖዶስ ተወግዞ የተለየው አእመረ አሸብር በአርባ ምንጭ ከተማ በጫሞ ቀበሌ በግለሰብ መኖሪያ ቤት ውስጥ ከግብረ አበሮቹ ጋር ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳት በመጠቀም ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ ክክርስቶስ ሥጋና ደም ጋር የማይገናኝ ተራ ነገር በማቅረብ “ሥጋ ወደሙ” ነው በማለት፣ የመጾር መስቀል በመጠቀም “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሄዱ እንደነበር ከሥፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

     ከዓርብ የካቲት ፰ ቀን ጀምሮ እስከ እሑድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጉባኤ ማዘጋጀታቸውንና ዓርብና ቅዳሜ የትምህርትና የምክክር ጉባኤ፣ እሑድ “ቅዳሴ” እናካሒዳለን በማለት ቀደም ብለው በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በለቀቁት ማስታወቂያ እንዲሁም ከተማው ላይ ማስታወቂያ በባነር አሠርተው በይፋ መስቀላቸውን የዓይን እማኞች ገልጠዋል፡፡

         የሀገረ ስብከቱ የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ የአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ፣ የስብከተ ወንጌል ኃላፊዎች እንዲሁም ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በመሆን ወደ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሄድ ጉዳዩን አሳውቀዋል፡፡ ብፁዕነታቸውም ቅዳሜ የካቲት ፱ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም “የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳትን ስለማስከበር” በሚል ለሚመለከታቸው አካላት ጉዳዩን ትኩረት ሰጥተው መፍትሔ እንዲፈልጉ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት፣ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፖሊስ መምሪያ ጽ/ቤት በደብዳቤ አሳውቀዋል፡፡

   ብፁዕነታቸው ለሚመለከታቸው አካላት በላኩት ደብዳቤም ከዚህ ቀደም በኑፋቄያቸው በሀገረ ስብከቱ ተወግዘው የተለዩ ግለሰቦች ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት ቤተ ክርስቲያን ላይ በማላገጥና የራሷን የሆኑትን ቅዳሴዋንና ንዋያተ ቅድሳቷንና ከራሷ ያገኙትን መዓርግ በመያዝና በመጠቀም በ፲/፮/፳፻፲፩ ዓ.ም ፕሮግራም ሊያካሔዱ ማሰባቸውን ያስረዳል፡፡ ፕሮግራም እንደሚያካሄዱም በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በመልቀቅ ምእመናንና ቤተ ክርስቲያንን ያስቆጣ ድርጊት በአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሰበካ ጉባኤ የቀረቡ የሕዝብ አቤቱታዎች እንደደረሳቸው የገለጹት ብፁዕነታቸው የሚመለከተው አካል ለሰላም ሲባል ትልቅ ትኩረት በመስጠት መፍትሔ ሊሰጥ ይገባዋል በማለት አሳውቀዋል፡፡

ብፁዕነታቸው በተጨማሪም በዚሁ አቤቱታቸው “የዚህች ቤተ ክርስቲያንም ሆነ የሀገረ ስብከቱ አቋም ሰላምን መስበክ ነው” ያሉት ብፁዕነታቸው ከዚህች ቤተ ክርስቲያን እስከወጡ ድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱን መገልገያ ንብረቶች (ንዋያተ ቅድሳት) ሥርዓቷንም ሆነ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ያገኙትን መዓርጋት ሊተዉና የራሳቸውን እምነት ሊያካሔዱ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ የራሳቸውን ፕሮግራም ማካሔዱን እንደማይቃወሙና የቤተ ክርስቲያን የሆኑትንም ንብረቶች እና ሥርዓቶች ሊመልሱ ይገባል ብለዋል፡፡

እሑድ ጠዋት በቦታው መረጃው የደረሳቸው የሕግ አካላት ባለመገኘታቸው ከፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ ከሰበካ ጉባኤ እንዲሁም ከስብከተ ወንጌል የተውጣጡ አባላትና ወጣቶች እንዲሁም ምእመናን ተሰባስበው ቅዳሴ ወደሚያካሔዱበት ቤት በመሔድ ግለሰቦቹ ሲጠቀሙባቸው የነበሩትን ንዋያተ ቅድሳት እንዲመልሱ ቢጠየቁም ፈቃደኛ ባለመሆናቸው የለበሱትን ልብሰ ተክህኖ በማስወለቅ፣ ከበሮ፣ መስቀል፣ መጻሕፍትና ሌሎች ንዋያተ ቅድሳት ይዘው ወደ አርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሲመለሱ፣ የሕግ አካላትም በመድረስ ግለሰቦቹን በቁጥጥር ሥር በማዋል ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስደዋል፡፡

ሰኞ ጠዋት የችግሩን አሳሳቢነት በመግለጽ አስፈላጊና ሕጋዊ መንገድ ተከትሎ የቤተ ክርስቲያኗ ጥያቄ እንዲመለስ በማለት በብፁዕነታቸው የተጻፈው ሁለተኛ ደብዳቤ በመያዝ ለሚመለከተው አካል ቢያመለክቱም የሚመለከተው አካል ደብዳቤውን ተቀብሎ ጉዳዩ ከባድ በመሆኑ ከዞኑና ከከተማው ኃላፊዎች ጋር መመካከር አለብን በማለቱ ክስ እስካሁን አለመመሥረቱ ተገልጿል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ሲኖዶስ እያከናወነ ስላለው  ጥረት ሲገልጹ “ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያናችን መገለጫ የሆኑትን ያሬዳዊ ዜማና ንዋያተ ቅድሳት ለማስጠበቅ ውይይቶችን ሲያደርግ እንደቆየና በአሁኑ ወቅትም የአእምሮ ንብረት በሚል ኮሚቴ ተቋቁሞ በጥናት ላይ ይገኛል” ብለዋል፡፡ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከትም በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አማካይነት የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አዋቅሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ሥራዎችን እየሠራ እንደሚገኝ ለዝግጅት ክፍላችን ገልጠዋል፡፡

     በሕግ አካላት ቁጥጥር ሥር ውለው ከነበሩት ግለሰቦች ውስጥ አንዱ አእመረ አሸብር ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም የሊቃውንት ጉባኤ አባል የነበረና በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘ ግለሰብ  ነው፡፡ የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጠዋት ከፖሊስ ጣቢያ እንደተለቀቁም የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት እንዲከበሩ ሀገረ ስብከቱ          ለሚመለከታቸው አካላት የጻፈው ደብዳቤ

የነነዌ ሰዎች እምነት ንስሓና የጾም አዋጅ

 

መ/ር ቢትወደድ ወርቁ

ትንቢተ ዮናስ አራት ምዕራፎች ያሉት፤ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነሣ ትውልድ ሁሉ ሊማርበትና ራሱን ሊያስተካክልበት የተጻፈ ታላቅ የትንቢት መጽሐፍ ነው፡፡ በዚህ የነቢዩ ዮናስ መጽሐፍ የተጠቀሱት ነቢዩ ዮናስን ጨምሮ የነነዌ ሰዎች ፣ንጉሡ ፣ዮናስ በየዋህነት ከእግዚአብሔር ፊት ወደ ተርሴስ ሊኮበልልበት የተሳፈረበት መርከብ ባለቤቶች /መርከበኞች/ እና ሌሎች ፍጥረታት ዓሣ አንበሪው፣የባሕር ማዕበሉ፣እግዚአብሔር ነቢዩ ዮናስን ያስተማረበት ትልና ቅሉ ሁሉ የነነዌ ሰዎች በኃጢአት ምክንያት ከመጣባቸው የጥፋት ዋዜማ አንስቶ ከኃጢአት ተመልሰው መዓቱ በምሕረት ቊጣው በትዕግሥት እሰከ ተለወጠላቸውና ከቅጣቱም እስከዳኑበት ጊዜ ድረስ የነበራቸው ተግባርና እግዚአብሔር የሠራላቸው የቸርነት ሥራዎች የተገለጡበት መጽሐፍ ነው፡፡

  መጽሐፉም እያንዳንዱ ቢዘረዘር ትልቅ መጽሐፍም ሊወጣው የሚችል ከመሆኑ አንጻር ያን ወደ ቤተክርስቲያን መጥተን ሊቃውንቱንና መምህራንን በመጠየቅ እንዲሁም ሌሎች ምሥጢራትን የሚያብራሩ  ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ መረዳት እንችላለን፡፡ አሁን ግን ባለንበት ወቅት በግላዊ፤ ቤተሰባዊና ሀገራዊ አኗኗራችን ከገባንበትና ሊገጥመን ከሚችሉ ችግሮች አንጻር የነነዌ ሰዎችን ታሪክ መስተዋት አድርገን ራሳችንን እንመለከትበት ዘንድ ታሪካቸውን በአጭሩ መቃኘትና የንስሓ መንገዳቸውን መከተል ተገቢ ይሆናል ፡፡ በመጽሐፍ ያለው ታሪክ በሙሉ የተጻፈልን ለፍጹም ትምህርትና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀን እንሆን ዘንድ እንዲሁም ለተግሣጽ ልባችንንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ጥበብ ይጠቅማልና (፪ጢሞ ፫÷፲፮-፲፯)

                የነነዌ ሰዎች የጥፋት ዋዜማ

ለነነዌ ሰዎችና ለከተማይቱ ጥፋት ምክንያት ሊሆን የነበረው  ምን እንደነበር መጽሐፍ ሲነግረን “የእግዚአብሔር ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል መጣ፤ ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ ክፋታቸውም ወደፊቴ ወጥቶአልና፤ በእርሷ ላይ ስበክ”(ዮናስ ፩÷፪ )ይላል፡፡ የነነዌን ከተማ “ታላቂቱ ከተማ” ያሰኛት ብልፅግናዋና እድገቷ ብቻ ሳይሆን በሥሯ የነበሩ ሰዎች ይፈጽሙ የነበረው ታላቅ ክፋት ነበር፡፡ስለዚህም የነዋሪዎቿ ክፋት እግዚአብሔርን አሳዝኖት ከክፋታቸው እንዲመለሱ የክፋት ሥራቸውን እንዲተውና ንስሓ እንዲገቡ ይነግራቸው ዘንድ ነቢዩ ዮናስን ወደ እነርሱ እንዲሄድ ላከው ፡፡ ባዕድ አምልኮትንና ጣዖትን ማስፈን፤ ለጣዖታት መስገድና መሠዋት ፣ ጥንቆላን ማስፋፋት ፣ሥር እየማሱ ቅጠል እየበጠሱ የሰዎችን አኗኗር ማጎሳቆልና ማዘበራረቅ ፣በዘፈንና አስረሽ ምችው ሰክሮ ዝሙትንና ሌሎች የሥጋ ፈቃዳትን በራስና በሌሎች ላይ ማንገሥ ነው፤ (ገላ ፭÷፲፯-፲፱)፡፡  የኃጢአት ሥራ  ከእግዚአብሔር ይልቅ ደስታና ተድላን በመውደድ ለዚያም በሰዎች መካከል ጠብን ከመዝራትና እንዲጋጩ ከማድረግ አንስቶ የራስን ጥቅም ብቻ በመመልከትም ማታለልን ሰዎች የሚጠፉበትንም መንገድ መቀየስና ለዚያም ቀንና ሌሊት በመትጋት ወደ ፍጻሜ ማድረስ ነው፤(ምሳ ፮÷፲፮-፲፱)፡፡ ክፉ ሰዎች የሚጠፉበትንና እግዚአብሔር የሚያሳዝኑበትን ሐሳብ ንግግርና ተግባራትን አጠቃሎ ይይዛል፡፡

   ክፋትንም የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር  ዘንድ የተጠላ ነው፤ ዘዳ ፳፭÷፲፭፡፡  የነነዌ ሰዎችንም ለጥፋት ያቀረባቸውና ከተማይቱንም “በሦስት ቀን ውስጥ ትገለበጣለች” (ዮናስ ፫÷፬) እስከ መባል ያደረሳት ክፋታቸው ነው፡፡ ሰው ልቡናውን ከክፋት ካላራቀ ራሱም ይጠፋል፡፡ ክፋቱም በዙሪያው ላሉት ሁሉ ተርፎ ሌላ ጥፋትን ይወልዳል ፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በቀድሞው ዘመን ለእስራኤል ዘሥጋ ” ኢየሩሳሌም ሆይ ትድኚ ዘንድ ልብሽን ከክፉ ነገር እጠቢ”፤ (ኤር ፬÷፲፬ ) ማለቱም ለዚህ ነው፡፡ ዛሬም ከራሳችን አንስቶ ዙሪያችንን ስንመለከት እግሮቻችን ወደ ክፋት የሚሮጡ፤ እጆቻችንም ደምን ለማፍሰስ የሚፋጠኑና በራሳችንም የክፋት ሐሳብ እየተራቀቅን ጠቢባን ሆነናል የምንል ሰዎች በዝተናል (ምሳ ፩÷፲፮)፡፡ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት እንደተናገረውም “ከኃጢአታችን ተመልሰን ንስሓ ካልገባን ክፋታችን ይገድለናል”፤(መዝ ፴፫÷፳፩)፡፡ የነነዌ ሰዎች ጥፋታቸው እስኪነገራቸው ድረስ በኃጢአት ሥራ ጸንተው ይኖሩ እንደ ነበር፤ ዛሬም በክፉ ሐሳብ ንግግርና ተግባር ላይ ካለን እኛም በጥፋት ዋዜማ ላይ እንደሆን ልንረዳ ይገባናል ፡፡

                  የእግዚአብሔር ቸርነትና የንስሓ ጥሪ

የነነዌ ሰዎች በመጥፎ ምግባራቸውና ኃጢአታቸው ምክንያት ሊጠፉ ሲገባቸው የቸርነት ባለቤት አምላካችን እግዚአብሔር እንዳይጠፉ በነቢዩ ዮናስ አንደበት የቸርነቱን የንስሓ ጥሪ አሰምቷቸዋል፡፡ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የምነግርህንም ስብከት ስበክላት”(ዮናስ ፫÷፪) እንዲል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን እኛ ከኃጢአታችን ከተመለስን ከስሕተታችን ተምረን ለመታረምና ሕይወታችንን ለማስተካከል ከፈቀድን እንደ ወጣችሁ፤ እንደ ጠፋችሁና እንደ ረከሳችሁ ቅሩ አይልም፡፡ በበደላችንና በኃጢአታችን ካሳዘነው ይልቅ በኃዘንና በጸሎት ፍጹም በሆነ ንስሓ ከተመለስን ይደሰታል፡፡ እርሱ ብቻ ሳይሆን ቅዱሳን መላእክቱም በሰማይ ይደሰታሉ፤ “ንስሓ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ ምክንያት በሰማይ መላእክት ዘንድ ታላቅ ደስታ ይሆናልና”(ሉቃ ፲፭÷፲) እንደተባለ፡፡ ስለሆነም ዛሬም በገባንበት የጥፋት መንገድ ፣ ተመቻችተንና ተደላድለን እየኖርን ካለንበት የኃጢአት መንደር በመውጣት ንስሓ በመግባት ሰላማዊ አኗኗርንና መንግሥተ ሰማያትን ገንዘብ እንድናደርግ ያስተምረናል ፡፡ “ንስሓ ግቡ፤ ኃጢአትም እንቅፋት እንዳይሆንባችሁ ከኃጢአታችሁ ተመለሱ፤ የበደላችሁትን በደል ሁሉ ከእናንተ ጣሉ፤ አዲስ ልብና አዲስ መንፈስም ለእናንተ አድርጉ፤ የእስራኤል ቤት ሆይ ስለምን ትሞታላችሁ ? የሟቹን ሞት አልፈቅድምና ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ስለዚህ ተመለሱና በሕይወት ኑሩ” (ሕዝ ፲፰÷፴-፴፪ )እንዲል፡፡ዛሬም ቢሆን በኃጢአት እየኖርን የሚታገሠን ንስሓ እንድንገባ ነው፤ (፪ጴጥ ፫÷፱) ንስሓ ካልገባንም ቅጣት መምጣቱ የማይቀር መሆኑን ልብ ማለት ይገባናል፤(ሮሜ ፲፩÷፳፪)፡፡

የነነዌ ሰዎች መመለስ

የነነዌ ሰዎች ንስሓ እንደማይገቡና በልባቸው ትዕቢት ሞልቶ፤ ከጀመረ ይጨርሰኝ ካፈርኩ አይመልሰኝ፤ብለው በበደላቸው ጸንተው እንደሚኖሩ ሰዎች አልሆኑም ፡፡ ኃጢአታቸውና በደላቸው እንዲሁም ንስሓ ካልገቡ ሊመጣ ያለው ጥፋት ሲነገራቸው በዙፋን ካለው ንጉሥ በዐደባባይ እስካለው ችግረኛ ሁሉም በአንድነት ሆነው ነቢዩ ዮናስ የሰበከውን የንስሓ ስብከት በልቡናቸው አምነው ተቀበሉ፡፡ ማመናቸውንም ከንጉሣቸው ጋር በመሆን ለጾም አዋጅ በመንገር ገለጡ፡፡ እምነታቸውንና ጾማቸውንም በንስሓ አጅበው አለቀሱ፡፡በዚህም እግዚአብሔር ቊጣውን በትዕግሥት መዓቱን በምሕረት ለወጠላቸው ፡፡

 “የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁ ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፤ንጉሡም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጎናጸፊያውን አውልቆ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ” (ዮናሰ ፫÷፭-፮) ተብሎ እንደ ተነገረ፡፡ ኃጢአታቸውን አምነው ንስሓ በማይገቡ ሰዎች እግዚአብሔር “የወደቁ አይነሡምን ? የሳተስ አይመለስምን ? ምን አድርጌሃለው ብሎ ከኃጢአቱ ንስሓ የገባ የለም …”(ኤር ፰÷፬) በማለት ይገረማል፤ ይደነቃልም፡፡ የነነዌ ሰዎች ግን በእምነታቸው፤በንስሓቸውና በጾማቸው እግዚአብሔርን አስደሰቱት፡፡ በዚህም በሐዲስ ኪዳን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ንስሓ በማይገቡ ላይ እንደሚፈርዱ ሲመሠክርላቸው “የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሓ ገብተዋልና ብሏል”፤ (ማቴ ፲፪÷፵፩)፡፡ ስለሆነም ከጥፋት እንድንድን ከክፉ ሐሳባችን፤ ንግግራችንና ተግባራችን ተመልሰን ንስሓ እንግባ ፡፡ “የንስሓ ኃዘን መዳንን፤ የዓለምም ኃዘን ሞትን ያመጣልና”፤(፩ ቆሮ ፯÷፲) እምነትን፤ ንስሓንና እውነተኛ ጾምን ገንዘብ አድርገን ለክብር ለመብቃት እንድንችል እግዚአብሔር በቸርነቱ ይርዳን፤ እመቤታችንም በምልጃዋ፤ ቅዱሳንም ሁሉ በጸሎታቸው አይለዩን አሜን!!

ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ጋር የሚጻረር የሥልጣኔ ተጽእኖ

በሕይወት ሳልለው

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥነ ምግባርን፤ ጥበብን፤ ጽሕፈትን፤ ሥነ ጥበብንና ኪነ ሕንፃን የምታስተምር፤ አንድነትን፤ ፍቅርን እና መተሳሰብን የምትሰብክና ምእመናን ሰብስባ የምትይዝ የክርስቶስ ቤት ናት፡፡

ከጥንት ጀምሮ ቤተ ክርስቲያን የሀገር መሪም ነበረች፡፡ ልጆቿንም በሥርዓት ታሳድግና ታስተምር ነበር፡፡ ነገሥታት በቤተ ክርስቲያን ሕግ በሚመሩበት ወቅት ዜጎቿም በሥነ ምግባር የታነፁ ነበሩ፡፡ የአክሱምና የጎንደር ዘመነ መንግሥትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚያን ዘመን ጀምሮም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወደ ውጭ ሀገራትም ተስፋፍታለች፡፡

ከጥቂት ዓመታት በፊት የቤተ ክርስቲያን ቀኖና እና ትውፊት ያልሆኑ ሥርዓቶች  በተለይም የበዓላት አከባበርና የክርስቲያናዊ አለባበስ ላይ ሥልጣኔ ተፅዕኖ አሳድሯል፡፡ ለምሳሌ የልደት በዓል አከባበር መቀየር ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ የምዕራባውያን ተፅእኖ ካሳደረው የአመለካከት ለውጥ የተነሣ ያልተለመዱ ምግባሮችን ከፈረንጆች በመውረስ ከክርስትና ጋር የሚጻረር ሥርዓት መከተል የጀመሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ የገና ዛፍ በሚል ስያሜ፤ ፅድ መሰል ሰው ሰራሽ ዛፍ በማስጌጥ አላስፈላጊ ክብር እየሰጡ፤ እንዲሁም ክርስቲያናዊ ምግባሮችን በመዘንጋት አብዛኛውን ጊዜ ትኩረታቸውን የቴክኖሎጂ ምርቶች ላይ በማድረግ ግለኝነትና እራስ ወዳድነትን በመላበስ ከቤተሰብ ፍቅርና ከቀኖናዊ ሕይወት የራቁ በርካቶች አሉ፡፡ ከገና በዓል አከባባር ጋር ተያይዞም ከምዕራባውያን  የወሰዱትን ልምድ ማለትም፤ የገና አባትን በመምሰልና ለሕፃናት ማጫወቻ በአሻንጉሊት መልክ በመሥራት አላስፈላጊ ወጪ ከማውጣታቸው ባሻገር የእኛን ሥርዓት እንደሚበርዝ ባለማስተዋል የተሳሳተ መንገድ ይከተላሉ፡፡

የአለባበስ ሥርዓትን ስንመለከት ሥነምግባርን የሚገልፅ በመሆኑ ከክርስቲያናዊ አለባበስ ውጪ ከሆነ ሰውነትን የሚያዋርድ ይሆናል፡፡ የሰው ልጅ በክብሩ በገነት ሲኖር፤ ልብሰ ብርሃንን /የፀጋ ልብሱን/ ሲገፈፍበትና ራቁቱን መሆኑን ሲያውቅ ሰውነቱን ለመሸፈን ቅጠል ለብሷል፡፡ ሥልጣኔ ራቁት የሚያስኬድ ከሆነ የሰውን ልጅ ክብር ይገፋል፡፡ ክርስቲያናዊ አለባበስን የሚጻረር ልብስ፤ (ሴቶች  እኅቶቻችን የተቦጫጨቀ ሱሪ፤ ከጡታቸው በታች የሆነ ልብስ ሲያደርጉ፤ ወንዶች ደግሞ ሱርያቸውን መቀመጫቸው እስኪታይ ድረስ ወደታች በጣም ዝቅ አድርገው) ይለብሳሉ፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያንንና ትምህርተ ሃይማኖትን አለማወቅም ጭምር ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ያስተማረችን ሰውነትን የሚሸፍን፤ ረጅም ቀሚስ እና ነጠላ መልበስ ነው፡፡ ሴቶች አንዳንድ ጊዜ በጣም አጭር ነጠላ በመልበስ ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ ከግራና ቀኝ ትከሻቸው ላይ ለመልበስ በሚሞክሩ ጊዜ ስለማይበቃቸው ሲጨናነቁ እናያለን፡፡ ወንድ የሴት፤ ሴት ደግሞ የወንድን ልብስ ማድረግ ሕጉ ይከለክላል፤ (ዘዳ ፳፪-፭)፡፡ ካህናትም ይህንን ተግባር ላይ ለማዋል በቤተ ክርስቲያን ከራሳቸው ጀምሮ የአለባበስ ሥርዓትን መጠበቅ፤ ሌሎችንም ማስተማር፤ማሳወቅና መገሰፅ አለባቸው፡፡ ትውልዱ ከግማሽ ወደሙሉ ራቁትነት ከመሻጋገሩ በፊት ማስተማር ይገባል፡፡

የማስተማር ኃላፊነት የአለባቸው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት መሪዎች፤ የቤተ ክርስቲያን  አገልጋዮች እንዲሁም ወላጆችና ቤተስቦቻቸው ናቸው፡፡ በልጆችና ወጣቶች ምግባረ ብልሹነት ተጠያቂ በመሆናቸው መገሰፅ፤ ማስተማርና ትክክለኛውን ሕግ ማሳወቅ ያስፈልጋል፡፡

ወደ ቅደስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ለማስቀደስና ጉባኤ ለመካፈል ሲመጡ ክርስቲያናዊ አለባባስ መልበስ እንዳለባቸው ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ነገር ግን ካህናቱም ቢሆን ደፍረው አይገስፁም፡፡ በዚህም የተነሣ አንዳንድ የነፍስ ልጆች የሌላቸው ካህናት እንዲሁም የንስሐ አባት የሌላቸው ክርስቲያኖች ኃላፊነታቸውን ለመወጣት አልቻሉም፡፡ እውነቱን መንገር ግን ያስፈልጋል፡፡ መጽሐፉ “ሕዝቤ ዕውቀት በማጣቱ ጠፍቷል” ይላል (ሆሳዕ ፬፥፮)፡፡

የአለባበስ ሥርዓትን ለማስተካካል ኃላፊነት ያለባቸው የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ብቻ ሳይሆኑ ወላጀችም ጭምር በመሆናቸው ሕገ ቤተ ክርስቲያን የሚፈቅደውን የአለባበስ ሥርዓት ለልጆቻቸው ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የመንፈስ ቅዱስ ልጁን ጢሞቴዎስን አርአያ እንዲሆን መክሮታል፤ (፩ኛጢሞ ፬፥፲፪)፡፡

የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣቢያ በህንድ ሀገር ፭ተኛ ዙር ሐዊረ ሕይወት አደረገ

         ሕይወት ሳልለው

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ  የማኅበረ ቅዱሳን የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣብያ በህንድ ሀገር የሚኖሩ አባላቱንና ምእመናንን በማስተባበር ከጥር ፲፭ እስከ ጥር ፳፩ ቀን  ፳፻፲፩ ዓ/ም ወደ ኬሬላ ፭ተኛውን ዙር የሐዊረ ሕይወት ጉዞ አካሄደ፡፡

በአባ ጂኦ ዮሴፍ መሪነት ፺፱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች መንፈሳዊ ጉዞ አድርገዋል፡፡ በህንድ ኬሬላ ግዛት ኮታይም ከተማ ወስጥ በሚገኙ ቅዱስ ጊዮርጊስና የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን  ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ሴርያን ቤተ ክርስቲያን፣ የመነኮሳት ገዳም፣ ማር ባስልዮስ ገዳም እንዲሁም የኦርቶዶክስ ቲኦሎጂካል (ነገር መለኮት) ሴሚናሪ እና የማር ባስልዮስ ክርስቲያን የኢንጅነሪንግና ቴክኖሎጅ ኮሌጅንም በዋነኛነት ጎብኝተዋል፡፡

ኮትያም ወደሚገኘው ኦርቶዶክስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በተደረገው ጉዞ ላይ ለምእመናኑ፤ “የቤተ ክርስቲያን ምሥጢራት” በሚል ርእስ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ከህንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር ያነጻጸረ ትምህርት በዶ/ር ረጂ ማቲው ተሰጥቷል :: በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተማሪዎች የበገና መዝሙርና በህንዳውያን ዘማሪዎች በህንድ ቋንቋ የተዘጋጀ መዝሙር በጋራ ቀርቧል፡፡ በጉዞው ላይ የነበሩት አባ ኦ ቶማስም “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በባህልና በበርካታ ንዋያተ ቅድሳት የታጀበች ናት” ሲሉ አድነቀዋል፡፡  በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው ዘቫላካራ ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በቀድሞው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንደተጎበኘ አባ ጂኦ ለምእመናኑ አስታውቀዋል፡፡፡፡

ከማእከሉ በአውቶብስ ሦስት ሰዓት፤ በጀልባ አንድ ሰዓት ተኩል የሚፈጀው እና በደሴት ወደተከበበው የቅዱስ ቶማስ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጉዞም ያደረጉ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኗ በቁጥር ትንሽ አባላት እና ጥቂት አገልጋይ እንዳሏትም አስገንዝቧቸዋል፤ ከዚህ ባሻገር በቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በወቅቱ ሲጠቀሙበት የነበሩት ባህላዊ ቅርሶችና ንዋየ ቅድሳትን ጎብኝተዋል፡፡ የጉዞው ተሳታፊዎችም “ከቦታው በረከትን አግተኝናል” ሲሉም የምስክርነታቸውን ቀል ሰጥተዋል፡፡

በከበሮ፣ በጸናጽል፣ በመቋሚያና በበገና ህብር የቀረበው ያሬዳዊ ዝማሬ መርሐ ግብር ላይ ሰፊ ማብራሪያ የሰጠው መ/ር ሳምሶን ስለመሳሪያዎቹ ለህንድ አባቶችና ለምእመናን ገለጻ አድርጓል፡፡ ስለአጠቃላይ መርሐግብሩ ከተሳታፊዎች ሐሳብ ተሰብስቦ፣ የአጋጠማቸው ችግሮች ላይ ውይይት በማድርግና የመፍተሔ አቅጣጫ በመስጠት፣ ፭ተኛው ዙር ሐዊረ ሕይወት  በሰላም ተጠናቋል፡፡

 

 

በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ለስብከተ ወንጌል የሚሰማሩ ሰባክያነ ወንጌል ተመረቁ

 

                               ተመራቂዎች በከፊል

በእንዳለ ደምስስ

  በማኅበረ ቅዱሳን አዳማ ማእከል ሥር የሚገኘው የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት፤ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኀበራት ጋር በመተባበር በሁለተኛ ዙር ገጠር ተኮር የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ለ፰ ወራት በሂዲ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወካህን መልከ ጼዲቅ አብያተ ክርስቲያናት ያሰለጠናቸውን ፴፬ ተተኪ ሰባክያነ ወንጌል ጥር ፭ ቀን ፳፻፲ወ፩ ዓ.ም የአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህን፤የየአጥቢያዎቹ አስተዳዳሪዎች፣ በጎ አድራጊ ምእመናንና የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት በተገኙበት አስመረቀ፡፡

ሰልጣኞቹ ከ፲ አጥቢያዎች የተመለመሉ ሲሆን፣፱ የትምህርት አይነቶችን ሲከታተሉ መቆየታቸውን፣አብዛኛዎቹ ሰልጣኞችም ካህናትና ዲያቆናት መሆናቸው አቶ ሀብታሙ ዘውዱ የወረዳ ማእከሉ ሰብሳቢ በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት ገልጸዋል፡፡ካህናቱና ዲያቆናቱ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ስልጠናውን መውሰዳቸውም ለወደፊቱ ከስብከተ ወንጌል አገልግሎት በተጨማሪ የቤተ የመቅደስ አገልግሎትን ለማጠናከር መልካም አጋጣሚ እንደሆነና አብያተ ክርስቲያናቱም ለሥልጠና የሚሆኑ ቦታዎችን በማመቻቸት የነበራቸው ተሳትፎ ታላቅ እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡

“የሥልጠናው ዋና ዓላማ ምእመናን በሚያውቁት ቋንቋ በማስተማር ከነጣቂ ተኲላዎች ለመጠበቅ ነው፡፡ የሥልጠናው ሙሉ ወጪም ብር 123,348.90 (አንድ መቶ ሀያ ሦስት ሺህ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንትብር ከዘጠና ሳንቲም) በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የቀድሞ ግቢ ጉባኤ ተመራቂዎች የተሸፈነ ነው” ብለዋል፡፡ የቀድሞ ተመራቂዎቹ ያበረከቱት አስተዋጽኦ በአርአያነት የሚጠቀስ መሆኑን የጠቆሙት ሰብሳቢው ይህንን መልካም ተሞክሮ ሌሎችም ማኀበራት በመውሰድ ሊማሩበት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ለተመራቂዎቹ ባስተላለፉት መልእክትም “ሰልጣኞች ከምረቃ በኋላ ትምህርት በቃን ሳትሉ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እግር ሥር  ቁጭ ብላችሁ መማር፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይገባችኋል፡፡ ዋናው ዓላማችሁንም ባለመዘንጋት ስብከተ ወንጌል ባልተስፋፋባቸው ቦታዎች እየተዘዋወራችሁ ቤተ ክርስቲያን የጣለችባችሁን ኃላፊነት እንድትወጡ ይጠበቅባችኋል” በማለት በሪፖርታቸው አስገንዝበዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት ከግልና ከማኀበራዊ ጉዳያቸው ቅድሚያ ለሥልጠናው ልዩ ትኩረት መስጠታቸው፣ የአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት ለአገልግሎት የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላትና ለአጥቢያዎች መመሪያ በመስጠት ስልጠናው የተሳካ እንዲሆን ታላቅ አስተዋጽዖ ማበርከታቸውን በመግለጽ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

የወረዳ ቤተ ክህነቱ ሊቀ ካህን መልአከ ፀሐይ ቀሲስ እንዳለ ሐረገወይን ባስተላለፉት መልእክትም የወረዳ ማእከሉ ለስበከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት የሚሰጠውን አገልግሎት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ያሳሰቡ ሲሆን ለተመራቂዎችም “በቋንቋ ምክንያት የሚጠፋውን ትውልድ ከሞት ወደ ሕይወት የመመለስ አደራ አለባችሁ” ብለዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት፣ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኅበራት ጋር በመተባበር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ተተኪ ሰባኪያነ ወንጌል ለማፍራት ፕሮጀክት ቀርጾ በመጀመሪያው ዙር በድሬ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ከ፰ አጥቢያዎች የተመለመሉትን ፳፫ ሰልጣኞችን ለስምንት ወራት አሰልጥኖ የካቲት ፳፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በአባቶች ቡራኬ አስመርቋል፡፡

ምንጭ፤ምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 26ኛ ዓመት ቊ8ቅጽ 26ኛ ቊጥር 398 ከጥር 1-15 ቀን2011ዓ.ም

 

 

 

የምእመናን ተሳትፎ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት የጠበቀ ሊሆን ይገባዋል

                     

በሕይወት ሳልለው

የሰው ልጅ ሕይወት፤ድኀነት፤ሰላም፤ ፍቅርና ደስታ መገኛ እግዚአብሔር፤ ከሕገ ኦሪት ጀምሮ በሰጠን የድኀነት መንገድ፤ በመስቀሉ ላይም በከፈለልን መሥዋዕትነት የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ከጥንት ጀምሮ ምእመናንን በመሰብሰብና በማሰተባበር ሥርዓተ አምልኮን እንዲፈጽሙ ስታስተምር ኖራለች፡፡ በሕገ ወንጌልም አምላካችን በአስተማረን መሠረት የክርስቲያኖች መማፀኛ የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ልጆቿን በፍቅርና በሥርዓት እንድታሳድግ ፈቅዷልና በእምነት፤ እንድናከብራት የእግዚአብሔር  ፈቃድ ነው፡፡

 “በብሉይ ኪዳን ይኖሩ የነበሩ ምእመናን በሕገ ልቦና (ባልተጻፈ ሕግ) ይመሩ የነበሩ አበው እና በሕገ ኦሪት (በተጻፈ ሕግ) የነበሩ ቅዱሳን አባቶች አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር በማድረጋቸው የእግዚአብሔር ረድኤት ያልተለያቸው ነበሩ፡፡የሐዲስ ኪዳንን ስንመለከት “በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕር አምላክነት አምነው፤ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተጠመቁ ክርስቲያኖች ናቸው”፤ (የምእመናን ድርሻ በቤተ ክርስቲያን)፡፡

 አንድ አምላክ፤አንዲት ጥምቀት፤ አንዲት ሃይማኖት፤(ኤፌ4፥4) ይህን የክርስትና ሕይወት መርሕ መሠረት አድርገው የሚኖሩ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች፤ ለብዙ ዓመታት  ሥርዓተ አምልኮን በሚፈጽሙባት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሃይማኖት አባቶች፤ ከካህናት፤ እንዲሁም ከሌሎች አገልጋዮች ጋር የሚያደርጉት ሱታፌ እምነታችውን፤ሥርዓታቸውንና አምልኮታቸውን ለማጠንከር ይረዳልና፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያን መኖር ያስፈልጋል፡፡ አብዛኞቹ  ኦርቶዶክሳውያን  ምእመናን  ዓመታዊ ክብረ በዓላት ላይ ብቻ ነው፡፡

መንክር መኩሪያና ዳዊት ጌታቸው ጥር ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ የጥምቀት በዓልን በጃንሜዳ ሲያከብሩ ያገኘናቸው ወጣቶች ናቸው፡፡መንክር ጥምቀትን ከልጅነት ጀምሮ ስለሚያከብር በየዓመቱ ጃንሜዳ ይመጣል፡፡“በዘንድሮ በዓል በበገናውና መሲንቆ፤በመዘምራንንና መዝሙሮች የቀደመውን ሥርዓት የበለጠ ወድጄዋለው፡፡አገልጋዩቹም ባሕልና ትውፊታቸንን ይዘው በመቅረባቸው እናመሰግናቸዋለን”፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ትውፊት፤ሥርዓትና፤ቀኖና በዓላትን ከማክበር በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት በተገቢው የመፈጸም ኃላፊነት እንዳለብን ያስታውሰናል፡፡ ወጣት  መንክር “አንዳአንድ የአስተዳዳር ችግር በመኖሩ ቅር ብሎኛል፡፡ካህናት እንዲሁም ሌሎች አገልጋዩች እኛን ሰብስበው አልያዙንም ከዘመኑ ጋር የመራመድ መሠረታዊ ችግር አለ፡፡ በዓልን ለማክበር ብቻ መገናኘት በቂ  አይደለም፡፡ የሃይማኖት አባቶች በጎቻቸውን  ተግተው መጠበቅ ይኖርባቸዋል”፤ሲል ቅሬታውን ገልጿል፡፡ዳዊትም ይህንን ሀሳብ በመጋራት “የአከባበር ሥርዓቱ ደስ ቢልም፤ የካህናትና የምእመናንን ኅብር ለበዓል ብቻ መሆን የለበትም፡፡ካህናት የሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማበረታታና ድጋፍ መስጠት አለባቸው”፡፡ ብሏል

አስተባባሪዎችና ሌሎች የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች አስፈላጊውን አገልግሎት በበዓላት ቀንና በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በወቀቱ እንደሚሰጡ ቢታመንም፤እነዚህ ችግሮች ሊከሰቱ የቻሉት በአስተዳደር ችግር መሆኑን እንደ መንክር ያሉ ግለሰቦች ይናገራሉ፡፡

 የቅዱስ ጳውሎስ የሐዲስ ኪዳን መምህር መጋቤ ሐዲስ አእምሮ ደምሴ ስለዚህ ጉዳይ አነጋግረናቸው ነበር፡፡ እሳቸውም “ጉድለቶች አይጠፉም፡ የምእመናን ሱታፌ ለመጨመር ሁሉም የየድርሻቸውን መወጣት አለበት፡፡የካህናቱ ድርሻ መቀደስ፤ ማስተማርና  እና መዘመር በመሆኑ ከምእመናኑ ጋር ኅብር ለመፍጠር የሚቻለው ምእመናን የምስጋናንና፤የመዘመርን ሥርዓት ሲያዘወትሩ ነው” ይላሉ፡፡ሆኖም ግን ትምህርተ ሃይማኖትን በበቂ ሁኔታ አለመማርና አለመተግበር በወጣቱ ላይ ያመጣው አሉታዊ ተፅእኖ እንዳለም ጨምረው ገልጸዋል፡፡ በማኀበር የተደራጁ ወጣቶች ስሕተት መሆኑን ባለመረዳት ቅዱሳት ሥዕላትን ባልሆነ ቦታ ላይ የሚለጥፉና ለማስዋቢያ የሚጠቀሙ እንዳሉም ታይቷል፡፡ነገር ግን እነዚያ ቅዱሳት ሥዕላት በክብር ቦታቸው ሆነው የሚጸለይባቸው ስለሆኑ ተገቢ ባልሆነ ስፍራ መታየት እንደሌለባቸው በአጽንዖት አሳስበዋል፡፡

 “በቲሸርትና ሌሎች አልባሳት ላይ ቅዱሳት ሥዕላትን ማሳተም ትክክል አይደለም፡፡ ምክንያቱም ልብሱ ሊቆሽሽ፤ሊቀደድና ሊጣል ይችላል፡፡እነዚያ ሥዕሎች ቅዱስ በመሆናቸው ለበረከት ብለን የምናደርገው ወደ መርገም እንዳይለወጥብን ለቅዱሳት ሥዕላት ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፡፡የምናገለግለውንም አገልግሎት ያደበዝዝብናል፡፡ሌሎች ጹሑፎችን መጻፍ ለምሳሌ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክትን ማስተላለፍ ይቻላል” ይህ የግንዛቤ እጥረት የፈጠረው ችግር ለምእመናን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት  ሥርዓትና ትውፊት እንዳልሆነ ማስረዳት ይገባል፡፡እነዚህንም ወጣቶች ከስሕተት ለመመለስ የሃይማኖት መሪዎች የማስተማርና የመምከር ከባድ  ኃላፊነት አለባቸው፡፡

በሌላ በኩል ግን መጋቤ ሐዲስ  አእምሮ የበዓል አከባባር ላይ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን የማገልገል ሥራ በራሳቸው ተነሳሽነትና ለበረከትም የሚያደርጉትን ተግባር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የጠበቀ እንዲሆን በማስገንዘብ፤ በዐበይት በዓላት አከባባር ላይ ከአዲስ አበባ ጅምሮ እስከ ገጠር ቤተ ክርስቲያን ድረስ ወጣቱ የሚሰጠው አገልግሎት በአስተማሪነቱ የሚወሰድ መልካም ተግባር ነው፡፡ታቦታት ወደ ማደሪያቸው ከመድረሳቸው አስቀድመው አካባቢውን በማጽዳት፤ ሕዝቡን በመቀስቀስ፤ታቦታቱ የሚያርፉበትንና የሚጓዙበትን መንገድ በማስዋብ፤ ምንጣፍ በማንጠፍና ቄጤማ በመጎዝጎዝ፤ አቧራንና ድካምን ችለው ሲያገለግሉ ይውላሉ” ሲሉ የወጣቶችን ተሳትፎ በአድናቆት ይገልጹታል፡፡