ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ፡፡

በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን፡፡

ጥር  17 ቀን  2011 ዓ.ም

እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ፡፡ / 1ኛ ጴጥ 4፤7/

በማንኛውም የሰው ልጅ ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችንና ግድያዎችን ሁሉ እናወግዛለን፡፡  በየቦታው የተከሰቱ ችግሮች እንዲቆሙም በድርጊቱ የሚሳተፉ አካላትን ሁሉ እንማጸናለን፤  እናሳስባለንም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን

የክርስትና ሃይማኖት ማእከላዊ ጉዳዩ ሰው ነው፡፡ አምላክ ሰው ሆነ፣፤ ሰውም አምላክ ሆነ፣ የሚለው የትምህርቱ አስኳል ዋና ነጥብም የሚያመለክተው የነገራችን ሁሉ ማእከል ሰው መሆኑን ነው፡፡ ይህም ለሰው ሲባል አምላክ እንኳ ራሱን ዝቅ አድርጎ በተዋሕዶ ሰው ሆኖ መገለጡንና በዚሀም ሰውን ከወደቀበት ማንሣቱን፤  ከዚያም በላይ ሰውን በተዋሕዶ ለአምላክነት ክብር ማብቃቱን የሚገልጽ ትምህርት ነው፡፡ ስለዚህ  ሀገራዊ ብቻ ሳይሆን ዐለምአቀፋዊ ሆነው በትልቁ የሚከበሩት የአምላካችን ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤና ዕርገት ሁሉ ማእከላዊ ነጥባቸው ሰው ነው፡፡ ሁሉም ነገሮች አምላክ ለሰው ሲባል ያደረጋቸው ናቸውና፡፡

ሌሎች አስተምህሮዎች ሁሉ አሁንም ሰውን ለማስረዳት ሲባል የተለያዩ አርእስት ይሰጣቸው እንጂ ማእከላዊ ነጥባቸው አንድ ነው፤ የሰው ድኅነትና ደኅንነት፡፡ የአንድ ሰው ጽድቁም ኃጢአቱም የሚለካው ለሰው በሚያደርገው ወይም በሰው ላይ በሚያደርገው ነው ማለት ይቻላል፡፡ ስለዚህም በምድር ላይ ከሰው በላይ የከበረና ጥንቃቄ ሊደረግለት የሚገባው ምንም ፍጥረት የለም፡፡ በምድር ላይ ጥንቃቄና ዕርምት የሚወሰድበት ነገር ሁሉ የመጨረሻ ዓላማው ሰውን ለመጥቀም ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ከሰው የሚጣላ ከአምላኩም ከአጠቃላይ ከፍጡራንም ሁሉ ጋር የሚጣላ ይሆናል፡፡ በሰው ላይ ያልተገባውን ድርጊት የሚፈጽም ሁሉ በፈጣሪው ላይ የሚያደርግ መሆኑን መዘንጋት የለበትም፤ ፈጣሪ ሰው መሆንን በተዋሕዶ ገንዘብ አድርጎ ሰው ሆኖ ተገልጧልና በሰው የሚደረግ ሁሉ በእርሱ ላይ የሚደረግ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡

የክርስትና ሃይማኖት መምህራንና ተቋማት ዋና ዐላማና ተልእኮም ሊመነጭ የሚችለው ከዚህ መሠረታዊ የሰው ክብርና ዋጋ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ስለዚህ በየትኛውም የዓለም ክፍል በማንኛውም ሰው ላይ የሚፈጸሙ መጥፎ ተግባራት ይልቁንም ከሕግ ማሕቀፍ የወጡትንና በሴራና በተንኮል የሚፈጸሙትን እንደ ማኅበር አብዝተን እናወግዛቸዋለን፤ እንጸየፋቸዋለንም፡፡ ይልቁንም በሀገራችን በኢትዮጵያ ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ የመጣው ንጹሐንን ሰለባ እያደረገ ያለው የተቀነባበረና የተነጣጠረ የሚመስለው ጥቃት በእጅጉ የሚያሳስብ መሆኑ ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡

Read more

በቃጠሎ የወደመውን ቤተ ክርሰቲያን ለመገንባት እንቅስቃሴ ተጀመረ

 

በእንዳላ ደምስስ

ጥር 15 ቀን 2011 ዓ.ም በቃጠሎ የወደመውን የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያንን ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩን ሊቀ ኅሩያን መ/ር ወጋየሁ ደምሴ የባሌ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ዋና ጸሐፊ ገለጹ፡፡

“በቃጠሎው ቤተ ክርስቲያኑ ሙሉ ለሙሉ ወድሞ ነው የደረስነው፡፡ ሕዝቡም ከፍተኛ ሐዘን ነው የተሰማው፡፡ ሁላችንም ልባችን ተሰብሮ በዕንባ ስንራጭ ነበር፡፡ ነገር ግን ሕዝቡ አልቅሶ ብቻ አልተበተነም፡፡ዕንባውን አብሶ ገንዘብ የማሰባሰቡን ሥራ በመጀመር የመፍትሔ እርምጃ ነው የወሰደው፡፡” ሲሉ የገለጹት የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ ናቸው፡፡ሀገረ ስብከቱ ካህናቱን፣ የሰበካ ጉባኤ አባላትን፣ የወረዳ ቤተ ክህነት ተወካዮችንና የሀገር ሽማግሌዎችን በማሰባሰብ ዘጠኝ አባላት ያሉት የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ በማዋቀር ቤተ ክርስቲያኑን በድጋሚ ለመገንባት ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራው መጀመሩንና እስከ አንድ ሚሊዮን ብር ማሰባበሰብ መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡

ከገንዘብ በተጨማሪም ምእመናን የአንገት ሐብላቻውንና የጣት ቀለበታቸውን በመስጠት፣ እናቶች ከመቀነታቸው እየፈቱ በመንፈሳዊ ስሜትና ቁጭት አቅማቸው የፈቀደውን ያህል ማበርከታቸውን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡

ሙስሊሙ ኅብረተሰብም በቤተ ክርሰቲያኑ መቃጠል ከፍተኛ ሐዘን እንደተሰማውና በቦታው በመገኘት ገንዘብ በመለገስ፣ እንዲሁም የግንባታ እቃዎችን ለመስጠት ቃል በመግባት መሳተፋቸውን፣ ቤተ ክርስቲያኑን ለማሠራትም በመስጊድ ውስጥ ሙስሊሙን በማስተባበር ገንዘብ ለማሰባበስብ ጥረት እያደረጉ እንደሚገኙ የሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ዋና ጸሐፊ ተናግረዋል፡፡

“በዛሬው ውሏችንም ለተቋቋመው የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ እወቅና ለመስጠት ሰበካ ጉባኤው ለወረዳው ቤተ ክህነት፣ የወረዳ ቤተ ክህነቱም ለሀገረ ስብከቱ ደረጃውን ጠብቆ በደብዳቤ በመጠየቅ እውቅና ተሰጥቷቸዋል፡፡” ያሉት ሊቀ ኅሩያን መ/ር ወጋየሁ የባንክ ሒሳብ (አካውንት) በመክፈትም ሕጋዊነት ባለው አሠራር ገቢ የማሰባሰብ ሂደቱ እንደቀጠለ ገልጸዋል፡፡

አገልግሎትን በተመለከተም ቤተ ክርስቲያኑ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ስላለው ከሰበካ ጉባኤውና ከሕንፃ አሰሪ ኮሚቴው ጋር በመመካከር አዳራሹን በማመቻቸት ሙሉ የቤተ ክርስቲያኑ አገልግሎት ማለትም ኪዳንና ቅዳሴ ሳይቋረጥ መቀጠሉንና የቃጠሎውን መንስኤ በተመለከተም የሕግ አካላት እያጣሩ መሆኑን ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡

በባሌ ሀገረ ስብከት የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ተቃጠለ

በእንዳለ  ደምስስ

በባሌ ሀገረ ስብከት ሮቤ ከተማና አካባቢው ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የሚገኘው የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ጥር 15 ቀን 2011 ዓ.ም ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት ላይ ለጊዜው ባልታወቀ መንስኤ መቃጠሉን መ/ር ያሬድ ገ/ማርያም የወረዳው ቤተ ክህነት ጸሐፊ ገለጹ፡፡

የቃጠሎው መንስኤና የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ በመጣራት ላይ እንደሚገኝ የገለጹት መ/ር ያሬድ፤ ቤተ ክርስቲያኑ በቃጠሎው ምክንያት ሙሉ ለሙሉ መውደሙንና በአገልጋዮችና በአካባቢው ምእመናን ጥረት ታቦቱን ብቻ ማዳን መቻሉን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡ዝርዝሩን እንደደረሰን እናቀርባለን፡፡

 

በጥምቀት በዓል የሃይማኖት አባቶች የሰላም ጥሪያቸውን አስተላለፉ!

                                                                                                        ሕይወት ሳልለው
የጥምቀት በዓል አከባበር በጃንሜዳ እና በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በድምቀት በተከበረበት ቀን፤ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ለቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ባስተላላፉት መልእክት ላይ ምእመናን በተለይም ወጣቶች በፍቅርና በመቻቻል መኖር እንዳለባቸው አሳሰቡ፡፡“የዛሬ ፵ ዓመት የሆነውን ዓይነት አካሄድና ታሪካዊ ስሕተት እንዳትፈጽሙ ተጠንቀቁ! የምትሹትንና የምትመኙትን ማግኘት የምትችሉት አንድነትና ሰላም እስካለ ብቻ ነው፡፡ አርቆ በማየትና አስተውሎ በመራመድ፤በትዕግሥትና በመቻቻል ሳይሆን በኃይልና በጉልበት የምንፈልገውን ማግኘት እንችላለን ብላችሁ ከሆነ ሁሉንም ልታጡ ትችላላችሁና አስተውሉ!” በማለት ገልጸዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፤ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ ፤ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ፤እንዲሁም የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶክተር ኂሩት ካሣው፤ ረ/ፕሮፌሰር ነቢዩ ባዬ የአዲስ አበባ ከተማ ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እና ከተለያዩ ሥፍራዋች ለመጡ ምእመናን መልካም የጥምቀት በዓልን የተመኙት ፓትርያኩ፤ ይህ በዓል የንስሓ ጥሪ መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ››፤ብሎ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እንዳስተማረን፤በዚህ አስከፊ ዘመን የንስሓን አስፈላጊነት መረዳትና መተግበር እንዳለብን አሳስበዋል፡፡
በዓለ ጥምቀት በዋነኛ የመዳን ሥርዓት መጀመሪያ መሆኑና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥር ፲፩ ቀን በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ እኛ እንድንጠመቅ እንዳስተማረን ‹‹ወውእቱ ያጠምቀክሙ በመንፈስ ቅዱስ ወበእሳት፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤››ተብሎ በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፲፮ ላይ እንደ ተገለፀውም ለእኛ ድኅነት ሆኖልናል፡፡

‹‹ጥምቀት ማለት ሰፋ ያለ ትርጒም ቢኖረውም ምሥጢራዊ ትርጒሙን ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው መንፃት፤መለወጥ፤ መሻገር፤ አዲስ ሕይወት፤ አዲስ ልደት፤ አዲስ ምሕረት የሚሉትን ሐሳቦች ያመሰጥራል›› በማለትም ቅዱስ ፓትርያርኩ አብራርተዋል፡፡ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማርቶማ የሕንድ ማላንካራ ኦርቶዶክስ ሶርያ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ፤የቅዱስነታቸውን ሐሳብ በመደገፍ እንዲህ በማለት መልካም ምኞታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማርቶማ

‹‹ይህ በዓል የብርሃን በዓል ቢሆንም እኛ እንደምናውቀው ዓለማችን በድቅድቅ ጨለማ የምትገኝ ሲሆን ለዚህ ጨለማ ብርሃን ያስፈልገዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዓለም ተስፋ ናት፡፡ ምክንያቱም ይህን የመሰለ በዓል በየትኛውም ዓለም አይከበርምና፡፡እኛም በዚህ ታላቅ በዓል ወቅት በጸሎት ከእናንት ጋር ነን፤››በማለት ከማጽናናታቸውም በተጨማሪ በክርስቲያኖች መካከል መልካም የሆነና የጠነከረ ግንኙነት ሰላም እንዲኖር ያደረገ እግዚአብሔርን ዘወትር እንደሚያመሰግኑና እግዚአብሔር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንዲጠብቅልንና ኢትዮጵያን እንዲባርክ በመመኘት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚገባ ተገለጸ

 

ተመራቂ ደቀ መዛሙርት

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ

     የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚገባ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ገለጹ፡፡

ብፁዕነታቸው ይህንን ቃል የተናገሩት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በጎንደር ከተማ የደብረ ኃይል ወደብረ ጥበብ በዓታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ለሦስት ተከታታይ ዓመታት የአቋቋም ትምህርት ሲከታተሉ የቆዩ ፶፬ ደቀ መዛሙርት ጥር ፫ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. ሲያስመርቅ ባስተላለፉት መልእከት ነው፡፡

በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ የብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ረዳት ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን፣ደቀ መዛሙርቱ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ እጅ የአቋቋም የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ለደቀ መዛሙርቱ ባስተላለፉት መልእክት “እናንተ የምድር ጨው ናችሁ! ተመርቃችሁ ስትወጡ ብዙ ነገር ይጠበቅባችኋል፡፡ ጨው ሁናችሁ ዓለሙን የማጣፈጥ ኃላፊነት አለባችሁ” በማለት ተመራቂ ደቀ መዛሙርቱ በተማሩት ትምህርት ወንበር ዘርግተው በማስተማርና ለምእመናን ትምህርተ ወንጌልን በመስጠት በተለይም ለገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን በመድረስ የተጣለባቸውን አደራ እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

    ብፁዕነታቸው አያይዘውም “አሁን በዝታችሁ ትታያላችሁ፡፡ነገር ግን በአብያተ ክርስቲያናት ስትከፋፈሉ ቊጥራችሁ አነስተኛ ነው፡፡አሁንም ብዙ መሥራት፣መማር፣ ማስተማር እና የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት ይገባችኋል” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ በበኩላቸው “ህየንተ አበዊኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ፣ በአባቶችስ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ” በማለት የቅዱስ ዳዊትን ቃል መነሻ በማድረግ ለደቀ መዛሙርቱ ባስተላለፉት መልእክት “እናንተ ደቀ መዛሙርት የዓለም ብርሃን ናችሁ፣ከዚህ ወጥታችሁ  አብያተ ክርስቲያናትን ሀገራችሁን በቅንነት በተሰጣችሁ አደራ እንድታገለግሉ አደራ እንላለን” ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የአቋቋም ምስክር ጉባኤ ቤቱ መምህር መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን ያፈሯቸው ደቀ መዛሙርት የተማሩትን ትምህርት በተግባር ይተረጉሙ ዘንድ ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ በመግለጽ “እነዚህ ደቀ መዛሙርት ዛሬ ተመርቀዋል፤ነገር ግን እየለመኑ ተምረው እየለመኑ መኖር የለባቸውም፡፡በርካታ ደቀ መዛሙርት ከትምህርት ገበታቸው የሚሰደዱት ሥራ አላገኝም እያሉ ነውና እንደ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ሁሉ ቅዱስ ሲኖዶስ በየቤተ ክርስቲያኑ የሚመደቡበትን መንገድ ቢያመቻች ጥሩ ነው” ሲሉ አሳስበዋል፡፡

ክቡር መምህር መጋቤ አእላፍ  በጉባኤ ቤቱ የሚታየውን ችግር ሲያስረዱም “ማኀበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ዘመናዊ ቤት ሰርቶልናል ነገር ግን አሁንም የሠርከ ኀብስቱ እጥረት አሳሳቢ ስለሆነ ለተማሪው ፍልሰት ምክንያት እየሆነብን ነውና መፍትሄ እንሻለን፡፡ደቀ መዛሙርቱ የሚማሩት ከየሀገራቸው ትንንሽ ልጆችን እያስመጡ ልጆቹ በየመንደሩ በመንቀሳቀስ “በእንተ ስማ ለማርያም”ብለው ምግብ ያመጡላቸዋል፡፡እነሱ ደግሞ እነዚህን ልጆች ያስተምሯቸዋል፡፡ አብያተ ክርስቲያናት ለአብነት ትምህርት ቤቶች ከዚህ በላይ ትኩረት ሰጥታ መሥራት አለባቸው ”ሲሉ ገልጸዋል፡፡

 ማኀበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በ፳፻፰ ዓ.ም ሠርቶ ያስረከበ ሲሆን፣ ከሕንፃው በተጨማሪ ለ፶፭ ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው በየወሩ የ፫፻፹፭ ብር ድጋፍ ያደርጋል፤ ቤተ ክህነትም ለ፴ ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው ፹፬ ብር በየወሩ ይደጉማል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ያሠራው ሕንፃም ቤተ መጻሕፍት፣ ክሊኒክ፣ የመምህር ቢሮ፣ ምግብ ቤት፣ መማሪያ ክፍልና መኖሪያ ለደቀ መዛሙርቱ ማሟላቱም በደቀ መዛመርቱ የምርቃት መርሐ ግብር ላይ ተገልጿል፡፡

ጉባኤ ቤቱ በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ያፈራ ሲሆን፤ ለአብነት ያህል አለቃ ገብረ ሐና፣መሪጌታ ሐሴት፣መሪጌታ ገብረ ማርያም፣ መሪጌታ ገብረ ዮሐንስ፣ መሪጌታ አሚር እሸቱ፣ መሪጌታ ላቀው፣ መምህር ክፍሌ ወልደ ፃድቅ፣ መጋቤ አእላፍ ሄኖክ ወልደ ሚካኤል እና አሁን በማስተማር ላይ የሚገኙት መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ በጉባኤ ቤቱም ማኅተሙን ለማግኘት ከሁለት እስከ ሦስት ዓመት ይፈጃል፡፡ በጉባኤ ቤቱ ከ፪፻ ያላነሡ ደቀ መዛሙርት በትምህርት ገበታ ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ በየዓመቱም የደቀመዛሙርቱ ምርቃት አይቋረጥም፡፡

አሁን በማስተማር ላይ የሚገኑኙት መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን ከመጋቤ እእላፍ ሄኖክ ወልደ ሚካኤል በ፲፱፻፺፯ ዓ.ም ወንበሩን በመረከብ እስከ አሁን ድረስ ከ፲፻ በላይ የሚሆኑ የአቋቋም መምህራንን አፍርተዋል፡፡

በብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ እና በብፁዕ አቡነ ዮሐንስ ትምህርተ ወንጌል እና ቃለ ምዕዳን፣ በተጨማሪም በደቀ መዛሙርቱ ቅኔ እና ያሬዳዊ ወረብ ቀርቧል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም የሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የአብነት መምህራን እና ምእመናንም ተገኝተዋል፡፡

 

ወርኃ ጥርና የወጣቶች ሕይወት

ዲ/ን ወልደ ቂርቆስ ደሳለኝ

የወጣትነት ምንነትና ፈተናዎቹ

በዚህ ጽሑፍ የወጣትነት ምንነት፣ መገለጫዎች እና ተግዳሮቶቹ ላይ ትኩረት አድርገን እንመለከታለን፡፡ ወጣትነት ፈጣን፣ አካላዊ፣ ስሜታዊና ማኅበራዊ ለውጦች የሚሰተናገዱበት ከልጅነት ወደ ጎልማሳነት፣ ከጥገኝነት ራስን ወደ መቻል መሸጋገሪያ ድልድይ የሆነ የዕድሜ ክልል ነው፡፡ እነዚህን ለውጦች ተክትሎ በወጣቶች ጠባይ (ባሕርይ) ላይ የሚከሠቱ ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል፡- ከፍተኛ የሆነ የአቻ ግፊት ተጋላጭነት፣ የሥጋዊ ፍትወት ፍላጎትና ግፊት፣ ከመጠን ያለፈ ግትርነትና ግልፍተኝነት፣ የስሜት መለዋወጥ፣ ቀድሞ ለመረዳት፣ አስቸጋሪ የሆኑ አስተሳሰቦች እና አመለካከቶች፣ ወላዋይነትና ውሳኔ ለመወሰን መቸገር፣ ለፍልስፍና ብሎም ለማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ትልቅ ትኩረት መስጠት፣ ራስን ከሌሎች የዕድሜ አቻዎች ጋር ማወዳደርና ማነጻጸር፣ ከቤተሰብ ብሎም ከሌሎች በዙሪያቸዉ ካሉ ታላላቆች ቊጥጥር ተላቆ ነጻ የመውጣት ፍላጎት፣ ራስን የመቻል ከፍተኛ ፍላጎት ወዘተ ናቸው፡፡
ከላይ በተዘረዘሩት ማለትም ወጣትነት በራሱ ከሚያመጣቸው ፈተናዎች ወይም ተግዳሮቶች ምክንያት የዕድሜ ክልሉን ፈታኝ ያደርገዋል፡፡ ለዚህም ነው አበው ወጣትነት ከዐራቱ ባሕርያት መካከል የእሳትነት ባሕርይ የሚያይልበት ነው ብለው የሚያሰተምሩን፡፡ ከዚህ በላቀ ደግሞ የወጣቶች አካባቢያዊና ቤተሰባዊ ተፅዕኖ ችግሮቹን የበለጠ አባብሶ የወጣቶችን ቀጣይ ሕይወት አደጋ ላይ ይጥላል፡፡
ወርኃ ጥር በሀገራችንና በቤተ ክርስቲያናችን
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከመፍቀሬ ጥበብ ሰሎሞን “ለሁሉም ጊዜ አለው፤ ከፀሐይ በታችም ለሆነው ነገር ሁሉ ጊዜ አለው፡፡” (መክ.፫፥፩) የሚለውን መሠረት አድርጋ ዘመናትን በተለያዩ አዕዋዳት እና አቅማራት ከፋፍላ ከማስቀመጥና ከማሳወቅ ባለፈ የሀገራችንን የተፈጥሮ ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ በየክፍለ ዓመቱ (ወቅቶች) ሊከናወን የሚገባውን ተግባር በመዘርዘር በአበው ሊቃውንት አማካይነት በቃልና በጽሑፍ ትመክራለች፤ ታስተምራለችም፡፡ ምእመናንም ይህንን ድንቅ ትምህርት ተከትለው ለመንፈሳዊ እና ማኅበራዊ ጉዳዮች ማከናወኛ የሚሆኑትን ጊዜያት በወቅት በወቅት ከፍለው ይጠቀሙበታል፡፡
በአብዛኛው የሀገራችን ክፍል በወርኃ ጥር ክብረ በዓላት በደመቀ ሁኔታ የሚከበሩበት (ከበዓለ ልደት ጀምሮ ጥር ፲፩ በዓለ ጥምቀት፣ በበርካታ አድባራትና ገዳማት ዓመታዊ ክብረ በዓላት በተለያዩ ቀናት በአማረና በደመቀ ሁኔታ መከናወኑ)፣ እንዲሁም በርከት ያሉ የማኅበራዊ ጉዳዮች በስፋት የሚከናወኑበት ወራት ነው፡፡
በእነዚህም ምክንያት በወርኃ ጥር ወጣቶች መንፈሳውያን ነን የሚሉትም ሳይቀሩ ለተለያዩ ፈተናዎች ተጋላጭ ይሆናሉ፡፡ ይህ ደግሞ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “አንተ የዕውሮች መሪ በጨለማም ላሉት ብርሃን እንደሆንህ በራስህ የምትተማመን ከሆንህ ሰነፎችን ልባሞች የምታደርግ፣ ሕፃናትን የምታስተምር፣ ጻድቅና የምትከብርበትን የኦሪትን ሕግ የምታውቅ የምትመስል እንግዲህ ሌላውን የምታስተምር ራስህን ለምን አታስተምርም” (ሮሜ፪፥፲፱-፳፩) በማለት እንዳስተማረን አስቀድመን ራሳችንን በፈተና ከመውደቅ ልንጠብቅ ይገባናል፡፡
በዚህ ጽሑፍ መንፈሳውያን ወጣቶች ከሌላው ጊዜ በበለጠ በጥር ወር ከሚከበሩ በዓላት ጋር ተያይዞ ጥንቃቄ ሊያደርጉባቸውና ራሳቸውን በፈተና ተሰናክለው ከመውደቅ ይጠነቀቁ ዘንድ መሠረታዊ ጉዳዮችንና የመፍትሔ ሐሳቦችን ጠቅለል አድርገን እንመለከታለን፡፡
ችግሮቹ
፩. ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ማፈንገጥ
ቤተ ክርስቲያን በውስጧ ለሚከናወን ማንኛውም ተግባር ቅዱስ መጽሐፍን፣ ትምህርተ አበውን እና መንፈሳዊውን ትውፊት አብነት በማድረግ ሕገ ደንብና ሥርዓትን በዝርዝር አስቀምጣለች፡፡ ለዚህም ነው ሊቃውንት ቤተ ክርስቲያንን ስንዱ እመቤት በማለት የሚጠሯት፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ምሉዕ እና ስንዱ እመቤት ከሚያሰኟት ሀብቶቿ አንዱና ዋነኛው ደግሞ ስለ በዓላት አከባበር ያስቀመጠችው ዝርዝር ሥርዓት ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ወጣቶች በአፍላ ስሜታዊነት እና በሉላዊነት (ዘመናዊነት) ተጽእኖ ምክንያት በታላላቅ መንፈሳውያን በዓላት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ብሎም ከሀገር ባሕልና ወግ ያፈነገጡ መጥፎ ድርጊቶች በዓላትን በማሳመርና በማድመቅ ሰበብ ሲያከናውኑ እንታዘባለን፡፡ በዓላት በቤተ ክርስቲያን የራሳቸው ነገረ ሃይማኖታዊ ትርጓሜና ትውፊታዊ ሥርዓት አላቸው፡፡ ነገር ግን ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ወጣቶች ከበዓላቱ ምንነትና ትርጓሜ ይልቅ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ወደ ስሕተት እየወሰዱና መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሕይወታቸውን ፈተና ላይ የሚጥሉ ጉዳዮቸ ላይ ትኩረት ሲያደርጉ እንመለከታለን፡፡
ከእነዚህም መጥፎ ልማዶች መካከል፡- ያልተገባና ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ከዚያም አልፎ ከሀገር ባሕል ያፈነገጡ አለባበሶች፣ የበዓላቱን ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ጥቅም ከመመልከት ይልቅ ምድራዊና ባሕላዊ ጠቀሜታቸው ላይ ብቻ ትኩረት ማድረግ ላይ ያዘነብላሉ፡፡ ለመንፈሳዊ ሱታፌ እና ለሰማያዊ በረከት ከመትጋት ይልቅ በዓይነ ሥጋ ብቻ አይቶ መደሰትን፣ በልቶ፣ ጠጥቶና ጨፍሮ መዝናናትን ዓላማ አድርጎ ወደ ክብረ በዓላቱ መምጣት፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያንን የሚከተሉ ምእመናንን ከመንፈሳዊ ተመስጦ ማስወጣት፣ እንዲሁም ራሳቸውን ወደ ሥጋዊ ሐሳብና ዝሙት የሚመሩ ብሎም ለኃጢአት የሚያነሳሱ ዘፈንና ጭፈራዎች መብዛት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ሌላው በወርኃ ጥር በወጣቶች መንፈሳዊ ሕይወት ላይ የምንመለከተዉ ፈታኝ ችግር የአንዳንድ ወጣቶች “የድሮውን ዘመን አስብ፤ የልጅ ልጅንም ዓመታት አስተውል፤ አባትህን ጠይቅ ይነግርህማል፤ ሽማግሌዎችህን ጠይቅ፤ ይተርኩልህማል፡፡” (ዘዳ.፴፪፥፯) እንዲል መጽሐፍ የአበው መምህራንን ምክረ ቃልና ትእዛዝ በማዳመጥ በመንፈሳዊ ብስለትና ቀናዒነት ከማገልገል ይልቅ በስሜት፣ በማን አለብኝነትና በግልፍተኝነት ለማገልገል መነሳት ነው፡፡ ይህም ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ወደ ማፍረስና እና እኔ ብቻ ያልኩት ካልሆነ በሚል አኩራፊነት ስሜት ብዙ ወጣቶችን ከቤተ ክርስቲያን እያሸሸ ይገኛል፡፡ ከዚህ ይልቅ “የሰው ወርቅ አያደምቅ” እንዲሉ አበው የሌላውን ከመናፈቅ ለራስ ሀብትና ሥርዓት ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል፡፡
፪. ከመጠን ያለፈ ምግብና መጠጥ
ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ ደጋግሞ ካነሳችው ምክር አዘል ጉዳዮች አንዱ በመጠን ስለ መኖር ነው፡፡ “ዳሩ ግን የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቧል፤ እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ ትጸልዩም ዘንድ በመጠን ኑሩ” (፩ኛ ጴጥ ፬፥፯፤፰፥፭) እንዲል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ነገር ሁሉ በአግባቡና በመጠኑ ይሆን ዘንድ ዘወትር ትመክራለች፤ ታስተምራለች፡፡ እርግጥ ነው የሰው ልጅ ለቁመተ ሥጋ ምግብ ይመገብ ዘንድ ግድ ነው፡፡ ነገር ግን መብላት፣ መጠጣት ከመጠን ባለፈ ጊዜ በመጀመሪያ ድኃ ወገናችንን ያስረሳል፤ ከዚያም ከፍ ሲል ራስን ያስረሳል፤ ከሁሉም በላይ ግን በመጠን አለመኖር የእግዚአብሔርን ሀልዎት ያስዘነጋል፡፡ ሕዝበ እስራኤል ከዚያ ሁሉ ውለታና ስጦታ በኋላ የሊቀ ነቢያት ሙሴን ወደ ደብረ ሲና መውጣት ተከትሎ ከፈርኦን የባርነት ቀንበር ያወጣቸውን፣ ባሕር ከፍሎ ያሻገራቸውን አምላክ ረስተው ጣዖት አስቀርጾ ወደ ማምለክ የወሰዳቸው ከመጠን ያለፈ ምግብና መጠጥ መሆኑን መጽሐፍ መዝግቦልናል፡፡ (ዘፀ. ፴፪፥፩-፮)፡፡
በዘመናችን በተለይም በወርኃ ጥር ለክብረ በዓላት፣ ለጋብቻና ለሌሎች ማኅበራዊ ጉዳዮች የሚዘጋጁ ግብዣና ድግሶችን ተከትሎ አንዳንድ ምእመናን በተለይም ወጣቶች በመጠን ኑሩ ያለውን የሐዋርውን ምክረ ቃል በመዘንጋት ራሳቸውን ለዓለም ፈተና አሳልፈዉ ሲሰጡ ይስተዋላል፡፡ እንዲያውም “ዐሥር ጊዜ ካልበሉ፣ ጠጥተውስ ካልሰከሩ የት አለ ዓመት በዓሉ” የሚል ብሂልም ያለማቋረጥ ይጠቀሳል፡፡ ከዚህ ይልቅ “እጅግ ለሰበሰበ አልተረፈውም፣ ጥቂትም ለሰበሰበ አልጎደለበትም፡፡” (ዘፀ፲፮፥፲፯) ተብሎ እንደተጻፈ አብዝተን በልተን ከእግዚአብሔር ጋር ከመጣላት ሁሉንም በመጠን ማድረግ አንዱ የክርስትና መገለጫ ነው፡፡
፫.ለባዕድ ልማዶችና ሱሶች ተጋላጭነት
በወርኃ ጥር ለወጣቶች ፈተና ከሚሆኑ ታላላቅ ጉዳዩች መካከል አንዱና ዋነኛው ደግሞ ለባዕድ ልማዶችና ሱሰኝነት መጋለጥ ነው፡፡ የተለያዩ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ወጣቶች መጤ ልማዶችንና ሱሰኝነትን የሚቀላቀሉት ወይም የሚጀምሩት በማኅበራዊ ጉዳዮች ምክንያት የሚዘጋጁ እንደ ሠርግ ያሉ የበዓላት ግብዣና ድግሶች ላይ ነው፡፡ በአቅራቢያችን ያሉ በሱስ የተጠመዱ ወጣቶችን ወደ አልኮል፣ ጫት፣ ሺሻ ወይም ሐሺሽ መጠቀምን እንዴት እንደገቡ ብንጠይቅ የምናገኘው ምላሽ ይኸው ነው፡፡
በዘመናችን ከማኅበራዊ ሚድያ ማደግና ከቴክኖሎጂ መዘመን ጋር ተያይዞ የዓለም ሀገራት አንድ መሆንና ልማዶች መወራረስ መጀመራቸውን መመልከት ይቻላል፡፡ ለዚህም ከጋብቻና ከወሊድ ጋር በተያያዘ የሚወራረሱ ልማዶች ትልቅ ማሳያ ናቸው፡፡ በሀገራችንም ነባሩ ባሕላዊው፣ መንፈሳዊውና ትውፊታዊው የጋብቻ ሥርዓት (ሠርግ) እየተዘነጋ አልያም እየተበረዘ የጥንት ማንነትና ትርጉሙን እያጣ ይገኛል፡፡ በተለይ ወጣቶች ከመንፈሳዊውና ባሕላዊው ሥርዓት ይልቅ ለምዕራባውያን የሠርግ ሥርዓቶች ትኩረት በመስጠት መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ውስጥ ራሳቸውን ሲከቱ ይስተዋላል፡፡ በዚህም ምክንያት ወጣቶች ለጊዜው ነፃነትና ዘመናዊነት የሚመስሉ፤ ነገር ግን ሙሉ ሕይወታቸውን አሰናክለው፣ ንጽሕናቸውንም አጉድፈው ለከባድ ውድቀት ለሚዳርጉ ጎጂ ሱሶችና ልማዶች ተጠጋላጭ ይሆናሉ፡፡
፬.መጠጥ፣ ጭፈራ፣ ስካርና ዝሙት
ከላይ የተጠቀሱት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ያፈነገጡ ልማዶች ባስከተሉት ተጽዕኖ ምክንያት ብዙ ወጣቶች በወርኃ ጥር በሚደረጉ መርሐ ግብሮች ወደ መጠጥ፣ ጭፈራ ብሎም ለስካርና ዝሙት ኃጢያት ይጋለጣሉ፡፡ በሉላዊነት ተፅዕኖ ምክንያት ሠርግን ከመሰሉ ታላላቅ ግብዣዎች አልኮል አለመጠጣት ጠጥቶም አለመስከርና ራስን አለመሳት፣ ከዚያም ከፍ ሲል ዝሙት አለመፈጸም በወጣቶች ዘንድ ያለመዘመንና የኋላ ቀርነት መገለጫ ተደርገው መወሰድ ጀምረዋል፡፡ በዚህም ምክንያት አንዳንድ ጠንካራ መንፈሳውያን ወጣቶች ሳይቀር ከዕድሜ እኩዮቻቸው ጋር ለመመሳሰል በሚል ሰበብ ሕይወታቸውን ወዳልተገባ አቅጣጫ ሲመሩና ተሰናከለው ሲወድቁ መመልከት የዘወትር ገጠመኛችን ከሆነ ሰነባብቷል፡፡
፭.ግጭትና ጠብ
በሌላ በኩል በወርኃ ጥር በሚከናወኑት ተደጋጋሚ የአደባባይ በዓላትና የሠርግ መርሐ ግብሮች መነሻነት ወጣቶችን የሚፈትነው ተግዳሮት ድንገታዊ ግጭት እና ጠብ ነው፡፡ በተለይም በአሁኑ ወቅት ባለው የሀገራችን የሰላምና የፖለቲካ አለመረጋጋት ወጣቶች በጭፍን ጥላቻ፣ በአፍላ ስሜታዊነትና በተዛባ መረጃ ተገፋፍተው ወደ ጠብ፣ ግርግር እና ግጭት የመግባት ዕድላቸው ከሌላው ጊዜ እጅግ የሰፋ ነው፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ አንዳድ ወጣቶች ለበዓለ ጥምቀት በሚወጡበት ጊዜ አስበውና ተዘጋጅተው ስለታም ነገሮችንና ባልንጀራቸውን የሚቀጠቅጡበት በትር (ዱላ) ይዘው ሲወጡ ስናይ በእውነቱ ታቦተ ሕጉን አጅበውና አክብረው በረከተ ሥጋ ወነፍስ ለማግኘት ሳይሆን ጦር ሜዳ ወርደው የሀገርን ዳር ድንበር የደፈረ ጠላትን ለማውደም ቆርጦ የተነሣ የጦር ሠራዊት ይመስላሉ፡፡ ይህ የጠብና ግርግር አጫሪነት ልማድ የሚለበሱ ቲሸርቶች ላይ ከሚያስቀምጡት ኃይለ ቃል ይጀምርና በሚጨፈረው የባህል ጭፈራ ዓይነትና የግጥም ይዘት ይቀጥላል፡፡ እነዚህ ጉዳዮች ሲታዩ ቀላል ቢመስሉም በጽሑፋችን መግቢያ ላይ ያነሳናቸውን የወጣትነት መገለጫዎች ጋር አያይዘን ለመረዳት ከሞከርን ከደረቅ ሣር ላይ ቤንዚን አርከፍክፎ እሳት ከመልቀቅ ይልቅ የከፋ ነው፡፡
መፍትሔዎች
ሀ/ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በአግባቡ መረዳት
ወጣትነት ከተጠቀምንበት ብዙ ኃይል፣ ትልቅ ተስፋ የአገልግሎት ትጋት ያለበት የዕድሜ ክልል ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን ለማስገንዘብ “በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ” (መክ.፲፪፥፩) እያለች ዘወትር ታስተምራለች፡፡ ብዙ ወጣቶች ይህንኑ የጠቢቡን ምክር በመከተል የወጣትነት ዘመናቸውን ለቤተ ክርስቲያን በመስጠትና በሰ/ት/ቤቶች በጽዋና የጉዞ ማኅበራት በመሰባሰብ ለቤተ ክርስቲያን በጎ ስጦታ ሲያበረክቱ ይስተዋላል፡፡
ነገር ግን በዘመናችን አንዳንድ ወጣቶች በቀናዒነት ተነሣስተው የሚያደርጓቸው ድርጊቶች ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ(ዶግማ) እና ሥርዓት (ቀኖና) የሚጣረሱና አንዳንዴም ከጥቀማቸው ጉዳታቸው የሚያይል ይሆናል፡፡ ይህም የሚመጣው በዋነኛነት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ ተምሮና መርምሮ ካለማወቅ ነው፡፡ ስለዚህ አገልግሎታችን “ያላዋቂ ሳሚ …” እንደሚሉት ተረት እንዳይሆንብን ጥረታችንም እግዚአብሔርን የሚያስደስት ቤተ ክርስቲያንንም የሚጠቅምና ራስንም የሚያንጽ እንዲሆን አካሄዳችንን ሁሉ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የተቃኘ ማድረግ ይገባናል፡፡ ወጣቶች ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በልማድና በወሬ ሳይሆን መጻሕፍትን በማንበብና መምህራንን በመጠየቅ ራሳቸውን ከጥፋት መታደግ ይኖርባቸዋል፡፡
ለ/ ከስሜታዊነት ወጥቶ በመንፈሳዊ ብስለት ማገልገል
ወጣትነት ስሜታዊነትና ችኩልነት የሚጨምርበት እርጋታና ማገናዘብ የማይታይበት ወቅት ነው፡፡ ብዙ የቤተ ክርስቲያን ወጣቶች ለአገልግሎት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲመጡ ከሚገጥማቸው ትልቅ ፈተና አንዱ ስሜትን ተቈጣጥሮ ራስን ገዝቶ ዝቅ ብሎ በትሕትናና በታዛዥነት ማገልገል አለመቻል ነው፡፡ መንፈሳዊ አገልግሎት ውጤታማ የሚሆነው መንፈሳዊ በሆነ አገልጋይ ሲከናወን ነው፡፡ መንፈሳዊ አገልጋይ ደግሞ አርምሞን፣ አስተዋይነትንና ታዛዥነትን ገንዘብ ያደረገ እንጂ በአጋጣሚዎች ሁሉ በስሜት ተገፋፍቶ ወደ ግጭትና ግርግር የሚያመራ አይደለም፡፡ ስለዚህ ወጣቶች በተለይ በዚህ በወርኃ ጥር በሚኖራቸው መንፈሳዊ ሱታፌ ቤተ ክርስቲያንን እንጥቀም:: እኛም ለበረከት እንብቃ ካሉ አገልግሎታቸውን በስሜትና በችኮላ ሳይሆን በመንፈሳዊ ብስለት፣ በትሕትናና በታዛዥነት የተዋጀ ሊያደርጉት ይገባል፡፡
ሐ/ ከመጥፎ የአቻ ግፊት መጠበቅ
የወጣትነት የዕድሜ ክልል የአቻ ግፊት የሚያይልበት፣ ከቤተሰብ የነበረን ቅርበትና ቁርኝት እየላላ ለዕድሜ አቻዎቻችን ያለን ቅርበት የሚጨምርበት ነው፡፡ በዚህ የዕድሜ ክልል ስንሆን ምሥጢሮቻችንና ወሳኝ የምንላቸውን ጉዳዮች ለቤተሰብ ከመንገርና ከማማከር ይልቅ ለዕድሜ ጓደኞቻችን ማጋራት ትልቅ ደስታ ይሰጠናል፡፡ ስለሆነም በዚህ ወቅት ወጣቶች በራሳቸው አስበውና አገናዝበው ከሚወስኗቸው ውሳኔዎች ይልቅ በጓደኞቻቸው ቀጥተኛና ተዘዋዋሪ ግፊት(ጫና) ተገፋፈተው የሚያሳልፏቸው ውሳኔዎች እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ በዘመናችን የሀገራችን በርካታ ወጣቶች በዕድሜ እኩያቸው ግፊት ከቤተ ክርስቲያን እየሸሹ፣ ከመንፈሳዊነት እየወጡ ወደ ዝሙትና ሱሰኝነት ሲወሰዱ እንመለከታለን፡፡ በዚህ በወርኃ ጥር ከላይ በዘረዘርናቸው ነገሮች ምክንያት ወጣቶች ከቤተሰብ ተለይተው በጋራ ሆነው የሚዝናኑባቸውና ለኃጢአት የሚጋለጡባቸው አጋጣሚዎች የበዙ ናቸው፡፡
ወጣቶች በቅድሚያ አብረዋቸው የሚውሉ ጓደኞቻቸውን ከመንፈሳዊና ትምህርታዊ ዓላማቸው አንጻር ሊፈትሹና ሊመርጡ ይገባል፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ በባልንጀራቸው ምክንያት የተጠቀሙ እንደተገለጹት ሁሉ በመጥፎ ባልንጀራቸው ምክንያት ወደ ክሕደትና ኃጢአት ያመሩ ሰዎች ጉዳይም በስፋት ተጠቅሶ እናገኛለን፡፡ ስለዚህ ወጣቶች ባልንጀራዬ ማነው? ብለው ራሳቸውን መጠየቅ ይገባቸዋል፡፡ በተለያዩ አጋጣሚዎች ጓደኞቻቸውን መምረጥ እንኳን ቢከብዳቸው መጥፎ የአቻ ግፊትን በመከላከል ለፈቃደ እግዚአብሔር እና ለሕይወት ግባቸው ቅድሚያ በመስጠት በንቃትና በቆራጥነት ለመጥፎ ተጽዕኖዎች አይሆንም እምቢ ማለትን ሊለማመዱ ይገባል፡፡
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ምስለ ጻድቅ ትጸድቅ ወምስለ ብእሲ ንጹሕ ንጹሐ ትከውን ወምስለ ጠዋይ ትጠዊ፤ ከጻድቅ ሰው ጋር ጻድቅ ትሆናለህ፤ ከቅን ሰው ጋርም ቅን ትሆናለህ፤ ከንጹሕ ሰው ጋር ንጹሕ ትሆናለህ፤ ከጠማማም ጋር ጠማማ ትሆናለህ፡፡” (መዝ፲፯፥፳፬) በማለት እንዳስረዳን ማንኛውም ሰው ውሎውን ካላስተካከለ አወዳደቁ የከፋ ይሆናልና ጓደኞቻችንን መምረጥ ያስፈልጋል፡፡ በጓደኛ ተጽዕኖ ሕይወታቸው የተበላሸባቸው በርካታ ምሳሌዎችን ከመጽሐፍ ቅዱስ መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከነዚህም መካከል አምኖን ከኢዮናዳብ ጋር፣ ሶምሶን ከደሊላ ጋር ያደረጉት ጓደኝነት ሕይወታቸውን እንደጎዳው ተጠቃሽ ነው፡፡
መ/ ምን አለበት ከሚል አስተሳሰብ መጠንቀቅ
ሌላው ወጣቶች በወርኃ ጥር ፈታኝ የሆኑ ተግዳሮቶችን በድል ለመወጣትና ከውድቀት ለመዳን ሊያደርጉት የሚገባ የአስተሳሰብና የአመለካከት ለውጥ ማምጣት ነው፡፡ ብዙ ወጣቶች ወደ ጥፋት ጎዳና የሚመራቸው የውሳኔ አሰጣጥ ክህሎት ማነስ ወይም መዳከም ነው፡፡ ይህ ክህሎት ከአስተዳደጋችን፣ ከትምህርት ግብዓት ብሎም ከንባብ ሕይወታችን ጋር የተያያዘ ነው ፡፡ ከሁሉም በላይ ግን አስተሳሰባችንና አመለካከታችን በዚህ ጉዳይ ላይ ትልቅ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ በድኅረ-ሥልጣኔ ማኅበረሰብ አስተሳሰብ ላይ ጎልተው የሚታዩት ”ምን አለበት” ምን “ችግር አለው” እና “ልሞክረው” ዓይነት አመለካከቶች ውሳኔዎችን ከራሳችን ይልቅ ሌሎች ሰዎች በተጽዕኖ እንዲወስኑ ትልቅ መንገድ ከፋች ናቸው፡፡ እንደዚህ ዓይነት አመለካከቶች የአፍላ ወጣትነት ዕድሜም ላይ ያሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን ወደ ጥፋትና ውድቀት ሲወስዱ ይስተዋላል፡፡ ስለዚህ ምን አለበት፣ ሞት አለበት ነውና ወጣቶች ራሳቸውን ከዚህ ዓይነት አመለካከት ሊጠብቁ ይገባል፡፡
በአጠቃላይ ወጣቶች በዚህ በወርኃ ጥር ራሳቸውን ለጽድቅና ለመንፈሳዊ በረከት የሚያበቁባቸው አጋጣሚዎች ብዙ ቢሆኑም ፈተናዎችም የሚበዙበት ወቅት ነው፡፡ ስለሆነም በዚህ ወቅት ወጣቶች በመንፈሳዊ ብስለትና በማስተዋል ከተጓዙ የወጣትነት ዘመናቸውን እንደ ዮሴፍና ሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ለድል አክሊል ለመንግሥተ ሰማያት የሚያበቃ ማድረግ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን በስሜትና በትዕቢት እንዲሁም ባለማስተዋል ከተጓዙ ወጣትነታቸው በሕይወታቸውን ለጉዳት አሳልፎ ይሰጣቸዋል፡፡ ወጣቶች ከእንደዚህ ዓይነት ጥፋት ይድኑ ዘንድም የቤተ ክርስቲያን አባቶች መምህራን የሰ/ት/ቤት አባላትና አመራሮች እንዲሁም ቤተሰብ ድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ ሐመር መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁ.9 ጥር 2011 ዓ.ም.

እንኳን ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል፣ በሰላም አደረሰን/አደረሳችሁ

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

                                                  በሀገር ውስጥና በመላው ዓለም ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን በሙሉ፡-
ከሁሉ በማስቀደም፣ የዘመናት ባለቤት ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር አምላክ፣ በረከት የምናገኝበትን ፆም በሰላም አስጀምሮ በሰላም በማስፈፀም፣እንኳን ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል፣ በሰላም አደረሰን/አደረሳችሁ! በማለት፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ስር ተዋቅሮ፣ የቅድስት ቤተክርስቲያንን አገልግሎት ለማገዝ፣ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያደረገ ያለው ማኀበራችሁ፣ ማኀበረ ቅዱሳን፣ መልካም ምኞቱን ይገልጻል፡፡

ውድ ምእመናን! የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት፡- የድኀነታችን ተሰፋ ቃል የተፈጸመበት፤ ዓመተ ኩነኔ ተደምስሶ፣ ዓመተ ምሕረት የታወጀበት ዕለት በመሆኑ፤ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህን በዓል በየዓመቱ በታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት፣ ደስታና ድምቀት ታከብረዋለች፡፡

እግዚአብሔር ጊዜን ለእኛ የፈጠረ እንጂ፣ለእርሱ ዘመን የማይቆጠርለትና ቦታ የማይወሰንለት አምላክ ሆኖ እያለ፤ እኛን ለማዳን ከእናታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍፁም አምላክ፣ ፍፁም ሰው ሆኖ የተወለደበትን ይህን ዕለት በየዓመቱ እየቆጠርን የምናከብረው፡- የቸርነቱን ስራ እያደነቅን፣ በልደቱ ብርሃንነት ከተገኘው በረከት ተካፋይ በመሆን፣ በመንፈሳዊ ሕይወታችን የበረታን እንሆን ዘንድ ነው፡፡

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲወለድ፡-ሰብአ ሰገል ልዩ ልዩ ገጸ በረከቶችን ይዘው፣ በቤተልሔም እንደተገኙ ሁሉ፣ እኛም ክርስቲያኖች በአንድ ልብና በጋራ በመሆን፣ በተሰጠን ጸጋ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ልናግዝና ልንጠብቅ ይገባል፡፡እኛ ክርስቲያኖች በዓሉን፡- ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ለሰው ልጆች ድኀነትና ፍጹም ሰላም ሲል ወደ ምድር የመጣበትን በማሰብ የምናከብረው ስለሆነ፤ እያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር በተሰጠን ሰላም እየተጠቀምንና እርስ በእርሳችን እየተዋደድን፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ብሎም ለሀገራችን ፍሬ ያለዉ ተግባር እንድንፈጽም እግዚአብሔር ይጠብቅብናል፡፡

ውድ ምእመናን! የእግዚአብሔር ልጆች በመሆናችን፣ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ትእዛዛቱን አክብረን በቤቱ ውስጥ መኖር የሚጠበቅብን ስለሆን፣ መዳናችን ዘለዓለማዊነት ያለው ይሆን ዘንድ፣ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም የተመሰለችውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ስለመሠረተልን፣ በእርሷ መገልገልና ማገልገል፣ የመንፈሳዊ ሕይወታችን ብቸኛዉ መንገድ ስለሆነ፤ በፍጹም ትጋት ልንጠቀምበት ይገባል፡፡

ማኀበረ ቅዱሳንም፡-የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጅ በመሆን አገልግሎቷን እየፈፀመ ያለው፣ሁላችንም ያገኘነውን የእግዚአብሔር ልጅነት በማጽናት የሰማያዊው መንግሥት ወራሾች እንሆን ዘንድ ነውና፤ ማኀበሩ፡- ኃይለ እግዚአብሔርን፣ የአባቶችን ጸሎትና ብራኬ አጋዥ በማድረግ እንዲሁም የአባላቱንና የምእመናንን ዐቅምና ድጋፍ በማስተባበር እየፈጸመ ያለው አገልግሎት፣ እግዚአብሔር እንደፈቀደ፣ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች የምናፈራበትና በሥነ ምግባር ተኮትኩተው በማደግ ሀገራቸዉን በሥርዓት ማገልገል የሚችሉ ዜጋዎችን ማግኘት የምንችልበት ነው፡፡

በአጠቃላይም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እየተፈጸመ ያለው አገልግሎት፡-
 በዘመኑ ከሚፈለገዉ የቅድስት ቤተክርስቲያን ዘመኑን የዋጀ የአገልግሎት ተደራሽነት፣
 መጠናከር ካለበት አሠራር እንዲሁም
 መፈታት ካሉባቸዉ ፈተናዎችና ችግሮች አኳያ ሲታይ፣ በጣም ትንሽና ከሁላችንም ገና ብዙ የሚጠበቅ ነገር ያለ መሆኑን የሚያሳይ ነዉ፡፡

ስለሆነም ኀምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክም ነው፤ ለኀምሣ ሰው ግን ጌጡ ነው! እንደሚባለው፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሆነውን የማኀበሩን አገልግሎት፡ቀርበን በጉልበታችን፣ በጊዜአችንና በገንዘባችን እናግዝ፡፡ እግዚአብሔር በሰጠን ጸጋ እንደ እየአቅማችንና ተሰጥዎአችን በቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ዉስጥ በቃለ ዐዋዲዉ መሠረት እየገባን፣ ድጋፍና ተሳትፎ እናድርግ፣ በማለት ማኀበሩ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

በመጨረሻም፡-በቅዱስ ወንጌሉ፣ «በነገር ሁሉ ደስ ልታሰኙ ለጌታ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን» ተብሎ እንደተጻፈ፣ በዓሉን ስናከብር፡- እግዚአብሔር ሰላምን በሃገራችን እንዲያጸናልን በመለመን፣ የተቸገሩ ወገኖችን በማሰብ እና በፍፁም መንፈሳዊ ሕይወት በመመላለስ፣በረከት የምናገኝበት ይሁንልን በማለት ማኀበሩ ምኞቱን ይገልጻል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡