ምሥጢረ ሆሣዕና

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፳፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዐቢይ ጾም ስምንተኛው ሳምንት ‹‹ሆሣዕና›› ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ላይ ተቀምጦ በክብር፣ በምስጋና፣ በዝማሬ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱን የምንዘክርበት በዓል ነው፡፡ በዚህ ዕለት ከዋይዜማው ጀምሮ በመንፈቀ ሌሊት፣ በነግህ እና በሠርክ ጌታችን ወደ ኢሩሳሌም የመግባቱን ምሥጢር፣ ከሕዝቡ የቀረበለትን ምስጋና እንደዚሁም ኢየሩሳሌም በግርማው መደንገጧን የሚያስረዳ ቃለ እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያናችን በሰፊው ይነገራል፡፡

ይህ ምሥጢርም በቅዱሳት መጻሕፍት በልዩ ልዩ መንገድ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በዚህ ዝግጅት፣ በማቴዎስ ፳፩፥፩-፲፩፤ በማርቆስ ፲፩፥፩-፲፤ በሉቃስ ፲፱፥፳፰-፵ እና በዮሐንስ ፲፪፥፲፪-፲፭ በተጻፈው ኃይለ ቃል መሠረት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጁትን አንድምታ ትርጓሜ መነሻ በማድረግ ምሥጢረ ሆሣዕናን (ጌታችን በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም የመግባቱን ምሥጢር) የሚያስገነዝብ ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን ትከታተሉ ዘንድ በአክብሮት ጋበዝናችሁ!

ክብር ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው በልዩ ልዩ አገሮች እየተዘዋወረ ቃሉን በማስተማር ሕገ ወንጌልን መሥርቷል፤ ብዙዎችንም ለመንግሥቱ አቅርቧል፡፡ ቃሉን ለመስበክ ከተዘዋወረባቸው ቦታዎች አንዷ ደግሞ ኢየሩሳሌም ናት፡፡ የመሲሑን መምጣት ማለትም የእግዚአብሔርን ሰው መኾን የሰሙና ያመኑ እስራኤላውያን ክርስቶስን በዓይነ ሥጋ ለማየት ይጓጉ፣ መምጣቱንም ይጠባበቁ ነበር፡፡

አመጣጡ ግን እነርሱ በጠበቁት ልዩና ተአምራዊ መንገድ ሳይኾን በትሕትና ተፈጸመ፡፡ ሲወለድ በከብት በረት፤ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባም በአህያ ተቀምጦ ለእስራኤል ተገለጠ፡፡ ሰማይ ዙፋኑ፣ ምድር የእግሩ መረገጫ የኾነ ጌታ መላእክቱን አስከትሎ፣ በመባርቅትና በነጐድጓድ ታጅቦ ይመጣል ተብሎ ሲጠበቅ የትሑታን ጌታ መኾኑን ለማጠየቅ በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ በዚህ ጊዜ ኢየሩሳሌም ተረበሸች፤ ደነገጠች፡፡ አምላክን ባልጠበቀችው አኳኋን ተገልጦ አይታዋለችና፡፡

ወደ ጥንተ ነገሩ እንመለስና ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሊገባ በተቃረበ ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል ሁለቱን በፊታቸው ወደሚገኝ አገር ሔደው ከውርንጫዋ ጋር ታሥራ የሚያገኟትን አህያ ፈተው እንዲያመጡለት አዘዛቸው፡፡ የሰው ልጅ ከማዕሠረ ኀጢአት (ከኀጢአት ማሠሪያ) የሚፈታበት ጊዜ ደርሷልና፡፡ ይኸውም አምላካችን የመጣው የዓለምን ኀጢአት ለማስወገድ መኾኑን የሚያጠይቅ ነው፡፡ ‹‹ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘየአትት ኃጢአተ ዓለም፤ የዓለምን ኀጢአት የሚያስወግድ እነሆ የእግዚአብሔር በግ!›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፩፥፴፮)፡፡

አህያዋንና ውርንጫዋን ‹‹ለምንድን ነው የምትፈቷቸው?›› ብሎ የሚጠይቅ ካለም ‹‹‹ጌታቸው ይሻቸዋልበሉ፤ ያንጊዜ ያሰናብቷችኋል (ይተዋችኋል)›› አላቸው፡፡ በተፈጥሮ ጌታቸው ነውና ማለትም ፈጥሯቸዋልና ‹‹ጌታቸው›› አለ፡፡ ደግሞም እርሱ እናቶችን ብቻ ሳይኾን ልጆችን ጭምር ወደ ቤቱ ማቅረብ ይፈልጋልና፡፡ ይህም ጌታችን በኀጢአት ማሠሪያ የተያዙ ኀጢአተኞችን ለመፍታት ከፈቀደ ‹‹ለምን ይህን ታደርጋለህ?›› ብሎ የሚቃወመው አለመኖሩን ያስገነዝባል፡፡

አህያዪቱንና ውርንጫዋን በተመለከተ ማቴዎስ ሁለቱንም፤ ማርቆስ ደግሞ ውርንጫዋን ብቻ ነው የጠቀሱት፡፡ የማቴዎስን አጻጻፍ መከተል ለታሪኩ እንደሚያመች፣ ይህም እንደማይጣላና የምሥጢር ተፋልሶ እንደማያመጣ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን ይተረጕማሉ፡፡ ለዚህ ማስረጃ ሲያቀርቡም ማርቆስ አንድ ማለቱ (ውርንጫዋን ብቻ መጠቀሱ) ለመናገር በቂ ነው ብሎ በማሰቡ እንደ ኾነ፤ አንድም ማቴዎስ የሕዝብም (ያመኑ) የአሕዛብም (ያላመኑ) መምህር በመኾኑ ሁለቱንም (አህያዬቱንና ውርንጫዋን) እንደ ጠቀሰ፤ ማርቆስ ግን የአሕዛብ እንጂ የሕዝብ መምህር ስላልኾነ የአሕዛብን ምሳሌ ብቻ (ውርንጫን) እንደ አወሳ ሊቃውንቱ ያስረዳሉ (ማር. ፲፩፥፫)፡፡

ይህ ዂሉ የተደረገውም ማለት ጌታችን በአህያዪቱና ውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት የፈቀደውም ‹‹አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፥ እጅግ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፥ እልል በዪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ኾኖ በአህያም፥ በአህያዪቱም ግልገል በውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፤›› ተብሎ የተነገረው ቃለ ትንቢት የሚፈጸምበት ጊዜ ስለ ደረሰ ነው (ዘካ. ፱፥፱)፡፡ ትርጓሜ ወንጌል በሐተታው ወለት (ልጅ) የተባለች እስራኤል፤ ጽዮን ደግሞ ኢየሩሳሌም መኾኗን ያብራራል፡፡ አንድም ወለትን (ልጅን) እንዳለ መስሎ ጽዮን የተባለች ሕግ መኾኗን ይጠቅሳል፡፡ የምሳሌዉን ትርጕም ሲያስረዳም እናት ልጆቿን ሠርታ፣ ቀጥታ እንድታሳድግ ሕግም ሕዝቡን ሠርታ፣ ቀጥታ እንደምታኖር ይናገራል (ማቴ. ፳፩፥፬-፭)፡፡

ወደ ታሪኩ ስንመጣ ደቀ መዛሙርቱም እንደ አዘዛቸው አህያዬቱንና ውርንጫዋን ፈተው ለጌታችን አመጡለት፡፡ ልብሳቸውንም በጀርባዋ ላይ ጐዘጐዙለት፡፡ ኮርቻ ይቈረቍራል፤ ልብስ አይቈረቍርም፡፡ ጌታችንም የማትቈረቍር ሕግ (ሕገ ወንጌልን) መሥራቱን ለማጠየቅ ልብስ ጐዘጐዙለት፡፡ አንድም ልብስ ነውርን ይሠውራል፤ እርሱም ከባቴ አበሳ (በደልን በሥውር ይቅር የሚል) አምላክ ነውና ልብስ ጐዘጐዙለት፡፡ ጌታችንም በጥበቡ በሁለቱም አንድ ጊዜ ተቀምጦባቸዋል፡፡

በትርጓሜ ወንጌል እንደ ተጠቀሰው ከኢየሩሳሌም እስከ ቤተ መቅደስ ያለው ርቀት ዐሥራ ስድስት ምዕራፍ ይኾናል፡፡ ጌታችን ዐሥራ አራቱን ምዕራፍ በእግሩ ተጕዞ፤ ሁለቱን በአህያዋ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ሔዷል፡፡ በውርንጫዋ ላይ ተቀምጦ ደግሞ ቤተ መቅደስን ሦስት ጊዜ ዞሯል፡፡ ይህም የሦስትነቱ ምሳሌ ነው፡፡ ዐሥራ አራቱን በእግሩ መሔዱም ዐሥሩ፣ የዐሠርቱ ትእዛዛት፤ አራቱ የአራቱ ኪዳናት ማለት የኪዳነ ኖኅ (የኖኅ ኪዳን)፣ የክህነተ መልከ ጼዴቅ (የመልከ ጼዴቅ ክህነት)፣ የግዝረተ አብርሃም (የአብርሃም መገረዝ) እና የጥምቀተ ዮሐንስ (የዮሐንስ ጥምቀት) ምሳሌዎች ናቸው፡፡ አንድም አምስት ሺሕ አምስት መቶዉን ዓመት በአራት በአራት መቶ ቢከፍሉት ዐሥራ አራት ሊሞላ አንድ መቶ ይጐደለዋል፡፡ ዐሥራ አራቱ ምዕራፍ፣ ይህ ዘመን (አምስት ሺሕ አምስት መቶዉ) ሲፈጸም አምላክ ሰው እንደ ኾነ ያጠይቃል፡፡

ጌታችን በአህያ መቀመጡ ስለ ምን ነው ቢሉ ትንቢቱ፣ ምሳሌው ሊፈጸም ነው፡፡ እርሱ ባወቀ (በአምላካዊ ጥበቡ) ትንቢቱን አስቀድሞ አናግሯል፤ ምሳሌውንም አስመስሏል፡፡

  • ትንቢቱ፡- ‹‹ሠረገላዉንም ከኤፍሬም፥ ፈረሱንም ከኢየሩሳሌም ያጠፋል፤›› ተብሎ አስቀድሞ ተነግሯል (ዘካ. ፱፥፲)፡፡ የትንቢቱ ፍጻሜ ሲደርስ ጌታችን በፈረስና በሠረገላ ሳይኾን በአህያ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡
  • ምሳሌው፡- ቀድሞ ነቢያቱ ዘመነ ጸብዕ (የጦርነት ዘመን) የሚመጣ እንደ ኾነ በፈረስ ተቀምጠው፣ ዘገር ነጥቀው (የጦር ትጥቅ ይዘው)፤ ዘመነ ሰላም የሚመጣ እንደ ኾነ ደግሞ በአህያ ተቀምጠው፣ መነሳንስ ይዘው ይታያሉ፡፡ ጌታችን የሰላም አምላክ ነውና የሰላም ዘመን መድረሱን፣ ሰላምን ይዞ መምጣቱን ሲያስረዳ በአህያ ላይ ተቀምጦ ታየ፡፡

ምሥጢሩስ ምንድን ነው ቢሉ በአህያ ላይ የተቀመጠ ሸሽቶ ማምለጥ፣ አሳዶ መያዝ አይችልም፡፡ ጌታችንም ለሚፈልጉት (ለሚያምኑበት) እንደሚገኝ፤ ለማይፈልጉት (ለሚክዱት) እንደማይገኝ ሲያመላክት በአህያ ላይ ተቀምጦ ታየ፡፡ አንድም በንጹሓን መሃይምናን ላይ አድሮ እንደሚኖር ሲያጠይቅ ነው፡፡

አህያ፣ የእስራኤል ምሳሌ ነው፤ አህያ፣ የሠረገላ ቀንበር መሸከም እንደምትችል እስራኤልም ሕግ መጠበቅ የለመዱ ናቸውና፡፡ ውርንጫ፣ የአሕዛብ ምሳሌ፤ ውርንጫ፣ ቀንበር መሸከም እንደማትችል አሕዛብም ሕግ መጠበቅ ያልለመዱ ናቸውና (አልለመዱምና)፡፡ በሌላ በኩል አህያ፣ የኦሪት፤ ውርንጫ የወንጌል ምሳሌዎች ናቸው፡፡ አህያ የሠረገላ ቀንበር መሸከም እንደ መልመዷ ኦሪትም በዘመኑ የተለመደች ሕግ መኾኗን፤ ውርንጫ ቀንበር መሸከም እንዳለመልመዷ ወንጌልም በዘመኑ ያልተለመደች (አዲስ) ሕግ መኾኗን ያመላክታል፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ብዙ ሕዝብ ‹‹እንኳን አንተ፣ ተቀመጥህባት አህያም መሬት መርገጥ አይገባትም›› ሲሉ ልብሳቸውን በጎዳናው ላይ አንጥፈውለታል፡፡ ሌሎችም ቅጠል እየቈረጡ ከመንገድ ያነጥፉ ነበር፡፡ እግዚአብሔርን መያዝ እንደዚህ ያስከብራል፡፡ ከእርሱ መለየት (እርሱን መካድ) ግን ያዋርዳል፡፡ እርሱን በሕይወታችን ላይ ካስቀደምን በእርሱ ምክንያት ብዙዎች ያከብሩናል፡፡

ሕዝቡ ለጌታችን ልብስና ቅጠል ማንጠፋቸው ከኢዩ የንግሥና ታሪክ ጋር ተመሳሳይ ኾኖ ይጠቀሳል፡፡ ኢዩ ከእስራኤል ነገሥታት አንዱ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ ለንግሥና ሲመረጥ ቅብዐ መንግሥት የተቀባው በድንገት ነው፡፡ ታሪኩም እንዲህ ነው፤ ነቢዩ ኤልሳዕ ከደቂቀ ነቢያት አንዱን ጠርቶ ‹‹ቀርነ ቅብዑን ይዘህ ሒድ፤ ኢዩን ቀብተህ አንግሠውና ፈጥነህ ና፤ ከሰው ጋር አትነጋገር›› ብሎ ላከው፡፡ መልእክተኛውም የኤልሳዕን ትእዛዝ ተቀብሎ ወደ ኢዩ ሔደ፡፡ ኢዩንም በአደባባይ ተቀምጦ ከባልንጀሮቹ ጋር ሲጫወት አገኘውና መልእክት እንዳለው ነገረው፡፡ ኢዩም ‹‹ከእኛ ነው ከሌላ?›› ብሎ ቢጠይቀው ‹‹መልእክት እንዳደርስ ወደ አንተ ተልኬ መጥቻለሁ›› አለው፡፡

በዚህ ጊዜ ወደ እልፍኝ ይዞት ገባ፡፡ በዚያም ‹‹ከመዝ ይቤ አምላከ እስራኤልቀባዕኩከ ትንግሥ ላዕለ ሕዝብየ እስራኤል፤ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤በሕዝቤ እስራኤል ላይ ትነግሥ ዘንድ ቀባሁህ›!›› ብሎ የንግሥና ቅብዓትን ቀብቶት ተመለሰ፡፡ ኢዩ ወደ ባልንጀሮቹ በሔደ ጊዜም ‹‹መልእክተኛው ምን አለህ? ነገረን?›› ብለው አፋጠጡት፡፡ እርሱም ‹‹ትነግሣለህ ብሎ ቀብቶኝ ሔደ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹እኛስ ሌላ ምን እንሻለን?›› ብለው ከፊሉ ምንጣፍ አንጥፈውለታል፤ ከፊሉ መጋረጃ ጋርደውለታል (፪ኛ ነገሥት ፱፥፩-፲፩ )፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባም በዚህ አምሳል እስራኤላውያን ልብሳቸውን በጎዳናው ላይ አንጥፈዋል፡፡ ቅጠል እየቈረጡ ያነጠፉም ነበሩ፡፡ ቅጠሉ ሰሌን ከኾነ አብርሃም ይስሐቅን፣ ይስሐቅ ያዕቆብን፣ በወለዱ ጊዜ፤ እስራኤል ከግብፅ በወጡ ጊዜ፤ ዮዲት ሆሎሆርኒስን ድል ባደረገች ጊዜ ሰሌን ቈርጠው ይዘው ማመስገናቸውን ያስታውሳል፡፡ ደግሞም ሰሌን እሾኽ እንዳለበት ዂሉ ጌታችንም የኃይል፣ የማሸነፍ ምልክት (ሥልጣን) ያለው አምላክ መኾኑን ያመላክታል፡፡ ሰሌንን እሳት አይበላውም፤ ለብልቦ ይተወዋል እንጂ፡፡ ይህም የጌታችን መለኮታዊ ባሕርይ የማይመረመር መኾኑን ያስገነዝባል፡፡

ቅጠሉ ተምር ከኾነ ተምር ልዑል (ትልቅ)፤ ፍሬው አንድና በእሾኽ የተከበበ እንደ ኾነ ዂሉ ‹‹አንተም ልዑለ ባሕርይ (በባሕርይህ ከፍ ከፍ ያልህ) ነህ፤ ባሕርይህ አንድ ነው፤ አይመረመርም›› ሲሉ የተምር ቅጠል አንጥፈውለታል፡፡ ቅጠሉ ዘይት ነው ያሉ እንደ ኾነ ዘይት ጽኑዕ (የጸና)፣ ብሩህ (የሚያበራ)፣ መሥዋዕት ነው፡፡ እስራኤል የዘይት ቅጠል ማንጠፋቸውም ጌታችን ጽኑዐ ባሕርይ (ባሕርዩ የጸና)፣ ብሩህ እንደ ኾነ እንደዚሁም ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ዓለምን እንደ አዳነ ያመላክታል፡፡ በዕለተ ሆሣዕና በቤተ ክርስቲያን የዘንባባ ቅጠል የሚታደለውም ይህንኑ ምሥጢር ለማስታወስ ነው፡፡

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ በገባባት በዚያች ዕለት በእስራኤል የነበረው ደስታ የተለየ ነበር፡፡ ሕፃናት ሲመሩ አረጋውያን እየተከተሉ፤ አረጋውያን ሲመሩ ሕፃናት እየተከተሉ፤ ነቢያት ሲመሩ ሐዋርያት እየተከተሉ፤ በዐሥር ሺሖች የሚቈጠር ሕዝብ ጌታችንን ከፊትና ከኋላው ከበውት፤ ጻድቃን በቀኙ፣ ተነሳሕያን (ንስሐ የሚያስፈልጋቸው) በግራው አጅበውት እነዚህ ዂሉ ‹‹ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት ቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር ሆሣዕና በአርያም፤ ለዳዊት ልጅ መድኀኒት መባል ይገባዋል፤ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ (አምላክነቱን ገልጦ) በእግዚአብሔር ስም የመጣ እርሱ (ክርስቶስ) መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለበት፤ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን የሚያድል በሰማይ ያለ መድኀኒት እርሱ ነው›› እያሉ አመስግነውታል (መዝ. ፻፲፯፥፳፬-፳፮)፡፡

ከፈሪሳውያንና ከሕዝቡ መካከልም በዚህ ልዩ ምስጋና እና ደስታ ተበሳጭተው ‹‹መምህር ሆይ፥ ደቀ መዛሙርትህን ተቈጣቸው›› አሉት፡፡ ጌታችንም እነርሱ ዝም ቢሉ ድንጋዮች አፍ አውጥተው የሚያመሰግኑት አምላክ መኾኑን ነግሮ አሳፍሯቸዋል፡፡ በዕለተ ሆሣዕና ሕዝቡ ዂሉ ለጌታችን የቀረበዉን ምስጋና እና የነበረዉን ደስታ ዓይተው ተገረሙ፡፡ ከተማዪቱም ‹‹በዚህ አኳኋን የተገለጠ ይህ ማነው?›› ብላ፤ አንድም የፊቱ ብርሃን ፀሐይን ሲበዘብዝ (ከፀሐይ በላይ ደምቆ ሲያበራ) አይታ፤ የሕፃናትን ምስጋና ሰምታ ተረበሸች፤ ታወከች፤ ደነገጠች፡፡

በቀር እርሱን ዓይቶ ማን ተረጋግቶ ይቆምና! ጌታችን በትሕትና በተገለጠ ጊዜ ግርማው ይህን ያህል ካስደነገጠ በግርማ መለኮት፣ በክበበ ትስብእት ዳግም ለፍርድ ሲመጣ እንዴት ያስፈራ ይኾን? ያን ጊዜ የቅጣት ፍርድ ከመስማትና ከመደንገጥ እንድን ዘንድ ከኀጢአት ተለይተን በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን እንኑር፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – የመጨረሻ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፳ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹‹ኢየሱስም መለሰ፤ እንዲህ ሲል፡- እውነት እውነት እልሃለሁሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም››

ጌታ ይህንን እውነት ዝቅ አድርጎ እንዳይመለከተው በማሰብ አስቀድሞ የተናገረውን ነገር ደገመለት፡፡ በእርግጥ የእግዚአብሔር ቃል አዎ አይደለም ከሚለው አፍአዊ ነገር በዘለለ መልስን የሚጠይቅ ነው፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከመረዳት አቅሙ በላይ ቢኾንም ጌታ እንደ ገና መወለድ ትምህርቱ ላይ ጠንከር ብሎ ሔዷል፡፡ ያለዚህ ልደት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየትም ለመግባትም የሚያስችል መንገድ የለም፡፡ ሰው ከውኃና ከመንፈስ መወለድ አለበት ይላል፡፡ ስለምን ውኃን ይጠቀማል? ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብን ለማመልከት ነው (ሕዝ. ፴፮፥፳፭፤ ፩ኛ ቆሮ. ፮፥፲፩፤ ቲቶ. ፫፥፭)፡፡ ይህ ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብ በመንፈስ ቅዱስ የሚፈጸም ነው፡፡ እርሱ ብቻ ያጥባል ያነጻል ውስጣዊ ልባችንን አዲስ ያደርጋል፡፡ ጌታ በሰርግ ቤት ተገኝቶ ውኃውን ወደ ወይን በመቀየር በሰርጉ ቤት ለነበሩ ዕድምተኞች ደስታን እንደ ሰጠ በመንፈሱ የሰጠው ውጫዊ የሰውነት መታጠብ አይደለም፡፡

ይህ ውኃ ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣ ይጠጣ በማለት ለሳምራዊቷ ሴት የነገራት የሕይወት ውኃ ነው፡፡ በያዕቆብ ጉድጓድ ውስጥ እንዳለው ውኃ አይነት አይደለም ያዕቆብ፣ ልጆቹና፣ ከብቶቹ የጠጡት ውኃ የሚያረካው የሥጋን ጥማት ነው፡፡ ጌታችን የሚሰጠን ውኃ ግን የነፍስን ጥማት የሚያረካ ነው፡፡ አዲሱ ልደት በውኃ ውስጥ ብቅ ጥልቅ እየተባለ መፈጸሙ ሞትን የመቀበልና ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የመቀበር ምልክት ነው፡፡ ከእርሱ ጋር እንነሣ ዘንድ የግድ ያስፈልገናልና፡፡ ‹‹እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፡፡ ከሞቱ ጋር አንድ እንኾን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን›› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ፡፡€

ከውኃና ከመንፈስ መወለድ የአሮጌውን ሰው መሞትና የአዲሱን ሰው ትንሣኤ ይጠይቃል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የኾነውን አዲስ ሕይወትም መቀበል ነው፡፡ እርሱም የትንሣኤ መንፈስ ነው፡፡ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር የሚያደርገንን አዲሱን ሰው የመፍጠር ሒደት ነው፡፡ በፈጣሪያችን መልክ የተፈጠረውን አዲስ ሰው መመልከት ነው፡፡ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምነው መስቀሉን ሊሸከሙ የሚወዱ ወገኖች በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ ቅዱስ ስም መጠመቅ አለባቸው፡፡ ‹‹የጌታ ቃል ትርጕም ለኒቆዲሞስ ምንድን ነው?›› ብሎ ለሚጠይቅ ምላሹ ‹‹ጌታ ከሥጋ ትውልድ ወጣ ብሎ መንፈሳዊውን ትውልድ እንዲያስብ ሳበው›› የሚል ነው፡፡

ጌታችን ለኒቆዲሞስ እንዲህ በማለት የነገረው ይመስላል፤ ‹‹ኒቆዲሞስ ሆይ እየነገርሁህ ያለሁት ስለ ሌላ ልደት ነው፡፡ ስለምን ነው ንግግሬን ወደ ምድራዊ ነገር የምታወርደው? የምነግርህ ነገር ስለምን በተፈጥሮ ሕግ እንዲገዛ ታደርጋለህ? ይህ ልደት በሥጋ (በምጥ) ከሚደረገው ትውልድ የተለየ ነው፡፡ አጠቃላይና የተለመደ ከኾነ ልደት ራስህን አውጣ፡፡ እኔ ሌላ ልደትሚገኝበት መንፈሳዊ ዓለም ሾሜሃለሁና፡፡ ሰዎች ዂሉ ከዚህ አዲስ ልደት እንዲወለዱ እወዳለሁ፡፡ አዲስ ዓይነት ልደትን ይዤ ወደ ምድር መጥቻለሁ፡፡ ሰውን የፈጠርሁት ከምድር አፈርና ከውኃ ነበር፡፡ ይህ ያገለግለኛል ብዬ የፈጠርሁት ምርጥ ዕቃ የተፈጠረበትን ዓላማ ዘንግቶ አግኝቸዋለሁና እንደገና ከአፈርና ከውኃ ልሠራው አልፈቅድም እንደገና በውኃና በመንፈስ እንዲወለድ እፈቅዳለሁ እንጂ፡፡››

ከመካከላችን እግዚአብሔር ‹‹ሰውን እንዴት ከውኃ ፈጠረው?›› ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ ምላሹን የሚያገኘው ግን የሚከተሉትን ጥያቄዎች መመለስ ሲቻል ነው፤ ‹‹ሰውን እንዴት ከምድር አፈር አበጀው? ጭቃን እንደምን አድርጋችሁ ወደ ተለያየ ክፍል ትከፋፍሉታላችሁ? አጥንት፣ ነርቭ፣ የደም ሥር፣ የደም ቧንቧ ከየት ተሠሩ? ቆዳ፣ ደም፣ ጉበት ከየት ተሠሩ? ይህ ታላቅ ሥራ ለምን የተከናወነ ይመስላችኋል? የተለያየውስ ቀለም? እነዚህ ዂሉ ዓይነቶች ውሁዶች ከየት ተገኙ?›› እነዚህ ዂሉ ነገሮች የምድርም የጭቃም አካል አይደሉምና፡፡

ምድር ዘርን ስትቀበል እንዴት አድርገው ሥር ይሰዳሉ? ነገር ግን በእኛ አካል ውስጥ ሲኾኑ እነዚህ ዘሮች ይፈጫሉ፡፡ ምድር ዘርን ምን መግባ ዘር ፍሬ እንዲያፈራ ታደርጋለች? እንደ ገናስ ሰውነታችን እንዴት በእነዚህ ዘሮች ይገነባል? ምድር ውኃን ትቀበላለች፤ ወደሚያፈራ ወይንም ትቀይረዋለች፡፡ የእኛ ሰውነት ግን ወይንን ተቀብሎ ወደ ውኃ ይቀይረዋል፡፡ በአሳብ የምትሰጠው ፍሬ ሁሉ የእርሷ ውጤት መሆኑን በምን በምን በምን መንገድ ነው የሚለውን ግን ማስረዳት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ምድር በፍሬዋ ሰውነታችንን ታጠግባለች፤ በእግዚአብሔር ላይ ያለን እምነት ብቻ ነው እነዚህ ዂሉ ነገሮች የምድር ውጤቶች ናቸው ብለን እንድቀበል የሚያደርገን፡፡

እነዚህ ዂሉ ዓይነት ተጨባጭ ነገሮች በየቀኑ የሚከሠቱ ስለ ኾነ እምነት የሚይጠይቁ ናቸው፡፡ መንፈሳዊ የኾነው ጉዳይ በቂ ትኩረትና ቅድምና ማግኘት እንደሚኖርበት እንገነዘባለን፡፡ የማይንቀሳቀሰው ምድር ለእግዚአብሔር ፈቃድ መልስ ይሰጣል፡፡ ምድር የምትሸከመው ይህ ዂሉ ነገር የተገኘው ለዚህ ፈቃድ ነውና፡፡ በተመሳሳይ ኹኔታ ከመረዳታችን በላይ የኾነ ጽንፍ የያዘ ብዙ ምልክት ይፈጠራል፡፡ ከመካከላችን አንዱ፡- ‹‹ውኃ ለዳግም ልደት ለምን ያስፈልጋል?›› ብሎ ቢጠይቅ ምላሹ ‹‹ይህ ልደት አምላካዊ ጠቀሜታ አለው›› የሚል ነው፡፡ መቃብር፣ መቀበር እምነት፣ ሕይወትና፣ ትንሣኤ እነዚህ ዂሉ ምሥጢራት በጥምቀት ጊዜ የሚከናወኑ ናቸው፡፡ ጭንቅላታችንን ውኃ ውስጥ እንነክራለን፤ ወደ መቃብር እንደምንወርድ ዂሉ አሮጌውን ሰውነታችንን እንቀብር ዘንድ ጭንቅላታችንን ስናነሣ አዲሱ ሰው በተመሳሳይ ኹኔታ ይገኛል፡፡‹‹ከመንፈስ የሚወለድ እርሱ ማነውእንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዶ በአእምሮው መንፈስ ከሚታደስ ሰው በስተቀር፤››€ተብሎ እንደ ተጻፈ (ኤፌ. ፬፥፳፫)፡፡

በእርግጥ ይህ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ እንደ ገና የተወለደው ሰው ነው፡፡ ይህ በዘላለማዊ ሕይወት የመተማመን ውጤት ነው፡፡ ይህም በጥምቀት አማካኝነት የሚፈጸም ነው፡፡ በእርግጥም እንዲህ ዓይነት ሰው እንደ ምሕረቱ መጠን በአዲስ ልደት በሚኾነው መታጠብም በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ መንፈሳዊ ልጅነትን የተቀበለ ነው፡፡ በሌላ ንባብ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ ይላል፤ ‹‹በመንፈስ ቅዱስ ስም ትጠመቃላችሁ›› (ሐዋ. ፲፩፥፲፮)፡፡ ከውኃና ከመንፈስ ከተወለደ ወገን ውጭ በመንፈስ ቅዱስ የተጠመቀ ማነው? ለዚህም ነው ጌታችን ‹‹… ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለዳችሁ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት አይቻላችሁም›› በማለት በጥምቀት የምናገኘውን ልጅነትና ዘለዓለማዊ መንግሥት የነገረን፡፡

በምሥጢረ ጥምቀት የኀጢአት እሥራት ይፈታል፡፡ ስለዚህም ሕፃናት ሳይቀሩ ይጠመቃሉ፡፡€ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ይገባ ዘንድ አይቻለውምና፡፡ ጥምቀት ኀጢአታችን ዂሉ ያጥባል፡፡ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ መቅደስ እንድንኾን ያደርገናል፡፡ ሰማያዊ ተፈጥሮአችንን ያድሳል፡፡ ይህም በመንፈስ ቅዱስ ግብር የሚፈጸም ነው፡፡ በጥምቀት ሰው ከሰይጣን ኀይል ነጻ ይኾናል፤ ይህም በመንፈስ ቅዱስ የሚከናወን ነው፡፡ የተጠመቀውን ሰው የሚቀድስና የሚያነጻ መንፈስ ቅዱስ ነውና፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ሰው ላይ ሰይጣን የወደደውን ያደርግበት ዘንድ አቅሙ አይኖረውም፡፡ ሰው በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር አንድነትን ሲፈጥር እንደ ገና ከመወለዱ ባሻገር ክርስቶስን በዂለንተናው ይለብሰዋል (ገላ. ፫፥፳፯)፡፡ ይህ ምሥጢር በንባብ ብቻ የምንረዳው አይደለም፡፡ የፍቅር መግለጫ ነውና፡፡ ይህንን የምንረዳው ጌታ ሥጋችንን ተዋሕዶ እኛን ለማዳን ሲል በእኛ መጠን በመወለዱ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – ሦስተኛ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹‹ኢየሱስም መልሶ እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው››€

ኒቆዲሞስ ምልክትን ማድረግ ለክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደሆነ ለማመኑ ማሣያ አድርጎ ቆጥሮ ነበር፡፡ ምክንያቱም የአይሁድ ረበናት እምነትን ምልክት ከመሥራት ጋር አያይዘውታልና፡፡ ስለ ክርስቶስ ማንነት ለመመስከር ከዚህ ወንዝ ባሻገር ያቋረጠው የለም፡፡ ስለዚህ ጌታን በጎነት ያለው መምህር፣ የእግዚአብሔር ሰው አድርጎታል፡፡ እግዚአብሔር ይስሐቅን ‹‹አትፍራ፤ እኔ ከአንት ጋራ ነኝና›› (ዘፍ. ፳፮፥፳፬) እንዳለው ሰው ዓይነት አድርጎ ገምቶት ነበር፡፡ ወይም እንደ መበለቲቱ ልጅ ‹‹ኢያሱ ከሙሴ ጋር እንደ ነበርሁ ከአንተም ጋር እሆናለሁ›› (ኢያ. ፩፥፭) ያለው ዓይነት ነቢይ ነበር ጌታ ለኒቆዲሞስ፡፡ ሌሎች ብዙ አለቆችና ነቢያት ተመሳሳይ ልምድ ነበራቸው፤ ነገር ግን ኒቆዲሞስ ምንም እምነትን ይዞ ቢመጣም ከፈሪሳውያን ጠባብ አስተሳሰብ ልጓም እንዳይወጣ የሚያደርግ አእምሮ ነበረው፡፡ የተማረውም ይኼንን እውነታ ነው፡፡ በጌታና በኒቆዲሞስ መካከል የነበረው ውይይት የሚከተሉት ነጥቦች የትኩረት አቅጣጫዎቹ ነበሩ፤

፩. የዳግም ልደት አስፈላጊነት እርሱም ውስጣዊው ዓለም የተሻለ እንደ ኾነ የሚያሳይ ነው፤ ይኸውም የእግዚአብሔር መንግሥት ነው፡፡ ይህ አባባል በቅብጥ፣ በሶርያ፣ በላቲን በመጀመሪያይቱ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጽሑፍ የተካተተ ነው፡፡ ዮስጢኖስ፣ ቀሌምንጦስ ዘእስክንድርያ፣ ጠርጡለስ፣ አውግስጢኖስና፣ ዠሮም ለአብነት ይጠቀሳሉ፡፡ ጌታችን ኒቆዲሞስን እንደ ገና እንዲወለድ እንደጋበዘው ተረድቷል፡፡ ይህ አስደነቀው፡፡ አሳቡ በልቡ ውስጥ መዳህ ጀምሯል፡፡ ስለዚህም ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል?›› አለ፡፡

፪. አዲሱ ልደት ከላይ ነው ሰማያዊ ነው፡፡ ይህ ድርጊት በቅዱሱና በሰማያዊው የእግዚአብሔር መንፈስ ብቻ የሚፈጸም ነው፡፡ የሰውን አሳብ ዂሉ ያለፈ ስጦታ ነው፡፡

፫. አዲሱ ልደት የሚፈጸመው በውኃና በመንፈስ ነው፡፡

፬. ይህ ልደት በኀይል ያለ በነፍስ የተመሰለ ነው፡፡ ስለዚህ ማንም ምሥጢሩን ሊገነዘበው አይችልም፡፡

በአይሁድ ጽሑፍ እውነት የሚለው ቃል መደገሙ በእውነት ቅዱስ ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ጌታችን የሚናገረው ነገር በጣም ጠቃሚና ትኩረት የሚያሻው መኾኑን ለመናገር ይጠቀምበታል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርጋታ ለኒቆዲሞስ የገለጸለት ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ዘንድ መምህር መኾኑን ማመን ብቻውን በቂ አለመኾኑን፣ ተአምራቱንም ማድነቅና የተለዩ መኾናቸውን ማወቅ በራሱ ግብ አለመኾኑን ነው፡፡ በእርግጥም የሚያስፈልገው እንደ ገና መወለድ ነው፡፡ እርሱም ሰማያዊ የኾነ ልደት ነው፡፡ ሰማያዊ መንፈሳዊ የኾኑ ጉዳዮችን ለማየት ያስችላልና፡፡ በእናቱ ማኅፀን ያለ ፅንስ በዚህ ዓለም እየኾነ ስላለው ነገር የሚያውቀው ነገር የለም፡፡

በተመሳሳይ ኹኔታ አንድ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት መመልከት አይቻለውም፡፡ እንደ ገና ከተወለደ ብቻ ነው የአዲሱን ዓለም ብርሃን መመልከት የሚችለው፡፡ ሊያይ የሚለው ጌታችን አጽንዖት ሰጥቶ የተናገረው ግሥ ለእውነተኛ ክርስቲያን አስፈላጊ ነው፡፡ አዲሱን ልደት ያጣጥም ዘንድ ስለ ተወለደ እንዲመካ አይደለም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊመለከት ለመንግሥቱም እንደሚገባ ሊመላለስ ይገባዋል እንጂ፡፡ ይህ ማለት አእምሮውና ልቡ ሰማያዊ በኾነ ነገር ላይ ማተኮር አለበት ማለት ነው፡፡ ከሰማያዊ ሕግ ጋር አብሮ የሚሔድ ሕግን ያለማወላወል ሊከተል ይገባዋል፡፡ አዲስ ግብ፣ አዲስ ተስፋ አዲስ ኀይልን ገንዘብ አድርጎ፡፡

በአዲሱ ልደት ክርስቲያን በዓይነቱ የተለየ ኑሮን መኖር ይጀምራል፤ አሮጌውን የሰውነቱን ሕንጻ አፍርሶ መሠረቱ ክርስቶስ የኾነውን አዲስ ሕንጻ በማነጽ አሮጌው ሰዎችን ተወግዶ የክርስቶስን መልክ የያዘው አዲሱ ሰው ሊታይ ይገባዋል፡፡ አስቀድመን ኀጢአት ጥንተ ተፈጥሮአችንን ስላጠፋው፣ የልባችንም ጥልቅ በኀጢአት ተይዞ ስለ ኖረ፣ ሥጋውያን በሥጋ ሕግና ፈቃድም የምንመራ ኾነናል፡፡ የምንመራውም የመልካም ነገር ጠላት በኾነ በዲያብሎስ ነበረ፤ ስለዚህ አዲሱ ልደት ልንሸሸው የማይገባ ጠቃሚ ጉዳይ ኾኖ ቀርቧል፡፡ ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ›› የሚለው የጌታ ቃል ለዚህ እውነት ማሳያ ነው፡፡

የእግዚአብሔር መንግሥት ምንድን ነው? ከሰማያዊው መሲሕ ሌላ መመልከት እንደሌለብን የምታሳስብ መንግሥት አይደለችምን? በእኛ መካከል መንግሥቱን መሥርቶ ይኖራል፡፡ ከእርሱ ጋር አንድነትን ፈጥረን የምናየው፣ የምንኖረው ዂሉ ለዚህ ሕይወት እንደሚገባ ነው፡፡ እርሱ ቅዱስ ስለ ኾነ እኛም ቅዱሳን እንኾናለን፡፡ በእኛ የሚኖረው የእግዚአብሔር መንግሥት ትክክለኛ ትርጕምም ይኼው ነው፡፡ ጌታ ‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ›› አለ (ማቴ. ፬፥፲፯)፡፡ እንደ ገናም በእግዚአብሔር መንግሥት ያለንን ሥፍራ ሲናገር ‹‹መንግሥተ ሰማያት በመካከላችሁ ናት›› ብሏል (ሉቃ. ፲፯፥፳፩፤ ራእ. ፩፥፮)፡፡

ይህ መንግሥት ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ኅብረትን የምንፈጥርበት መንግሥት በመኾኑ እንዲህ ተብሏል፤ ‹‹የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የኾነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችም›› (ሮሜ. ፲፬፥፲፯)፡፡ ይህ መንግሥት ለዘላለማዊ ሕይወት ዋስትና ነው፡፡ ወደ ሰማይ እንድንጓዝ ጌታ በጌትነቱ ሲመጣ አስደናቂውን ክብር እንድንካፈል ያደርገናል፡፡ ከምንም በላይ አሳባችንን ከፍ ከፍ አድርጎ ውስጣዊ ነፍሳችንን የመጨረሻውን ቀን እንድትመለከት ጌታ ሲመጣ ሰማያዊ ዘውድን ደፍተን ያለ ፍርሃት በፊቱ እንቆም ዘንድ የሚያስችለንን ጸጋ እንይዝ ዘንድ ያስችለናል፡፡

የጌታን ቃል እንደ ገና በሌላ አባባል እንግለጠው ብንል ‹‹ዳግመኛ ካልተወለድህ ከመንፈስ ጋር ኅብረት ካልፈጠርህበጥምቀት ልጅነትን ካላገኘህ፣ እኔን በተመለከተ ትክክለኛ የኾነውን አሳብ አታገኝም›› የሚል ይኾናል፡፡ ኒቆዲሞስም ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?›› በማለት ጠየቀ፡፡ የኒቆዲሞስ ጥያቄ የእውቀት ድካሙን ይገልጣል፡፡ ጌታ የሚናገረው በመንፈሳዊ ቋንቋ ነው፡፡ የኒቆዲሞስ ልብ ነገሮችን የሚያገናኘው ቁሳዊ ዓለማዊ ከኾኑ ነገሮች ጋር ነው፡፡ ቁሳዊ ነገሮችን ከልቡናው ከአእምሮው ካላወጣ መንፈሳዊና ሰማያዊ የኾኑ ምሥጢራትን እንደምን ሊገነዘብ ይችላል? ያኔ ነው ወደ እውነት መድረስና በእግዚአብሔር መንፈስ አዲስ መንፈሳዊ ጉልበትን ይዞ ምሥጢርን መረዳት የሚቻለው፡፡

ይህ ዂሉ ነገር እያለ ኒቆዲሞስ ጀርባውን ለጌታ አልሰጠም፤ እርሱ የጎደለው አንድ ነገር እንዳለ አምኖ ትምህርቱን ቀጥሏል፡፡ በግብሩ ምንም እንኳን መምህርና አለቃ ቢኾንም በትሕትና እውነተኛ የኾነ ነገርን ለመማር የተዘጋጀ መኾኑን ገልጧል፡፡ ነገር ግን ጌታ የሚለው አዲስ ልደት የማይቻል እንደ ኾነ ገምቷል፡፡ አስደናቂ ሰው ነው፡፡ ረጅም ዘመን የትምህርትና የአመራር ልምድ ያለው ሰው ከጌታ እግር ሥር ተንበርክኮ አዲስ ነገርን ሲማር መመልከት ያስደንቃል፡፡ ለእውነተኛ አለቃ ጌታ የሰጠው ምሳሌ አስቸጋሪ ሊኾንበት ይችላል፡፡ አሁን ኒቆዲሞስ ስለ ትምህርትና ስለ አመራር ልምዱ ሲመካ አንመለከተውም፡፡ እስከ መጨረሻው እስትንፋሱ ድረስ ሲማር እንጂ፡፡ አምብሮስ እንዲህ ይላል፤ ‹‹የኒቆዲሞስኔታ የሚያሳየን መማር የማያስፈልገው እግዚአብሔር ብቻ መኾኑን ነው፡፡››

ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ መጣ፤ ከፍ ያሉ ነገሮችን አዳመጠ፡፡ እንዲህ ዓይነት ጉዳዮች ተራ ሰው የሚገልጣቸው አይደሉም፡፡ ማንም ሰውም ከዚህ አስቀድሞ ሰምቷቸው አያውቅም፡፡ በቅፅበት ኒቆዲሞስ ወደ ከፍታ ወጣ፤ ነገር ግን መረዳቱ ጨለማ ነበር፡፡ ነገር ግን በራሱ ማስተዋል ገና የቆመ በመሆኑ ሊሸከማቸው ስላልቻለ ወደቀ፤ የጌታን ቃል እንዴት ሊሆን ይችላል? በማለት ጠየቀ፡፡ ጌታ የተናገረውን ነገር እንዲያብራራለት ሰው ከሸመገለ በኋላ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን በማለት ማብራሪያ ጠየቀ፡፡ ኒቆዲሞስ ስለ መንፈሳዊ ልደት ሰምቷል፡፡ ነገር ግን በመንፈስ አልተለማመዳቸውም (አያውቀውም)፡፡ የተማመነውም ቁሳዊ መረጃ ላይ ነው፤ ይህን ትልቅ ምሥጢር ለመረዳትና ለመተርጐም ምሳሌ አድርጎ ያቀረበው የሰውን የሥጋ ልደት ነው፡፡ ይህን ኹኔታ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ በማለት ይገልጠዋል፤ ‹‹ለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም፡፡ በመንፈስም የሚመረመር ስለ ኾነ ሊያውቀው አይችልም›› (፩ኛ ቆሮ. ፪፥፲፬)፡፡

በዚህ ዂሉ ነገር ኒቆዲሞስ ክብርና ጉጉት ይታይበታል፡፡ ጌታ የነገረው ነገር አላስቆጣውም፡፡ ነገር ግን ይህ ኹኔታ የማይቻል መኾኑን አስቦ ጥያቄ ጠይቆ ዝም አለ፡፡ ሁለት ነገሮችን ተጠራጥሯል፡፡ ምን ዓይነት እንደ ገና መወለድ እና የእግዚአብሔር መንግሥት፡፡ አይሁድ በየትኛውም ጊዜ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የተናገሩት ነገር የለም፡፡ ስለ ዳግም ልደትም እንዲሁ፡፡ ስለነዚህ ነገሮች ሰምተውም አያውቁም፡፡ ኒቆዲሞስን ያስደነቀውም ነገር ይህ ነው፡፡

ቅዱስ አውግስጢኖስ እንደተ ተናገረው ይህ ሰው ከአዳምና ከሔዋን የሚደረግ ልደትን ሰምቷል፤ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለሚደረገው ልደት ግን አያውቅም፡፡ የሚያውቀው ዘርን የሚተኩ ወላጆች በሞት ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ ነው፡፡ ነገር ግን ሕይወትን ስለሚሰጠው ስለ አዲሱ ልደት ያለው ግንዛቤ ከመረዳት በታች ነው፡፡ ንብረታቸውን የሚወርሱ ልጆችን የሚወልዱ ቤተሰቦች ያውቃል፡፡ ነገር ግን ዘወትር የሚኖሩ ልጆችን የሚወልዱ የማይሞቱ ወላጆችን በተመለከተ እውቀት የለውም፡፡ ሁለት ዓይነት መወለድ አለ፡፡ አንደኛው በምድር የሚደረግ ሁለተኛው ሰማያዊ፡፡ የመጀመሪያው ከሥጋና ከደም ሁለተኛው ከውኃና ከመንፈስ፤ የመጀመሪያዎቹ ለሞት የተጋለጡ ናቸው የኋለኞቹ ዘላለማውያን ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የተወለዱት ከወንድና ከሴት የኋለኞቹ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ኒቆዲሞስን በተመለከተ የሚያውቀው አንድ ልደትን ብቻ ነው፡፡

ይቆየን

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – ሁለተኛ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ እየሔደ የመማሩ አምስተኛው ምክንያት ለካህናት አለቆች ወሬው ሊደርስ ይችላል ብሎ ከፍርሃት የተነሣ ነው፡፡

ስድስተኛው ደግሞ ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ መድረሱን አይሁድ ቢያውቁ ጌታችንን ለመዋጋት ቁጣቸውን ይጨምርላቸዋል፡፡ ኒቆዲሞስን ራሱን ለመጉዳት አይሁድ ፈሪሳውያን ሊነሣሡበት ይችላሉ፡፡ ምንም እንኳን በጌታ ትምህርት ቢማረክም በቀን እንዳይሔድ እምነት አንሶት ሊሆን ይችላል፡፡

ሰባተኛው ምክንያት ከምንም በላይ ጌታ የዓለም ብርሃን መኾኑን በእርግጠኝነት አለመረዳቱ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ ነው፤ የእስራኤል መምህር ነው፡፡ ሰማያዊውን ደስታ ገንዘብ ያደርግ ዘንድ አዲስ ልደት የሚያስፈልገው ሰው ነው፡፡ በምሽት ሲመጣ ደካማ የሆነ እምነትን ይዞ ነበር የመጣው፤ ነገር ግን የጌታ በር ተከፍቶ አገኘው፡፡ ጌታ ስሜቱን ሊጎዳው አልወደደም፡፡

ዂሉ ነገር የሚቆጠረው እምነት እንደ ሰናፍጭ ቅንጣት ቀስ በቀስ በልቡ ውስጥ እንደሚያድግ ነበር፡፡ ጌታ የፈለገው ያች ቅንጣት አብባ፣ አፍርታ፣ ጌታ በሚሰቀልበት ጊዜ ትልቅ ዛፍ ትኾን ዘንድ ነበረ፡፡ እንደዚያ ሲኾን ነው በዚያ እምነት ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው በድፍረት የጌታን ሥጋ የቀበረው፡፡

ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በተገናኘ ጊዜ የአይሁድ ድካም በእርሱም ላይ ይንጸባረቅ ነበር፡፡ አስቀድመን እንዳልነው በብርሃን ሳይኾን በጨለማ የመምጣቱም ምክንያት ይህ ነበር፡፡ ነገር ግን መሐሪው አምላክ አልጠላውም፤ ትምህርቱንም አልከለከለውም፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ከጌታው ጋር በፍቅር ለመነጋገር ቻለ፡፡ ጌታችንም ከፍ ያለውን ምሥጢር ገለጠለት፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከአይሁድ የተለየ ቢኾንም ጌታን የቆጠረው ሰው አድርጎ ነው፡፡ ይናገረው የነበረው እንደ ነቢይ ነው፡፡ ያደረገውን ምልክት እያደነቀ ነበር የጠየቀው፡፡ ‹‹መምህር ሆይከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን … እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከኾነ በስተቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና›› ነበር ያለው፡፡

ኒቆዲሞስ ጌታ በተናገረው አዲስ ልደት ተደንቋል፡፡ ልክ እንደ ሌሎች አይሁድ ዘመዶቹ የአብርሃም ዘር በመኾኑ የሚመካ ነው፡፡ ጌታ ደግሞ እንደ ገና ተወለድ እያለው ነው፡፡ አይሁድ ለእግዚአብሔር የተመረጡና የተወደዱ አድርገው ራሳቸውን ይቆጥሩ ነበር፡፡ በነቢያትና በተስፋው ቃል ኪዳን የተቀደሱ ሕዝቦች ነን ይሉ ነበር፡፡ ከምንም በላይ እግዚአብሔር ከእነርሱ አባቶች ጋር ቃል ኪዳን ገብቶ ነበር፡፡ ልዩ መቅደስና መሥዋዕትም ነበራቸው፡፡

ኒቆዲሞስ እስራኤላዊ ብቻ አልነበረም፤ ፈሪሳዊም ጭምር እንጂ፡፡ ምን ዓይነት ከዚህ የበለጠ ልደት ጌታ ይሰጠኛል ብሎ ሊያስብ ይችላል? አይሁድ መሲሑ ሲመጣ የእስራኤል መንግሥት እንደሚያምንበት እንደ ገናም እንደሚወለዱ ይገምታሉ፡፡ ነገር ግን አስቀድሞ በነበራቸው ኩራትና ትምክህት አንጻር ሲመዝኑት ይህ የሚኾን አይመስላቸውም ነበር፡፡ እነርሱ አሁን ከያዙት የአብርሃም ልጅነት የከበረ ልደት ያለ መስሎ አይታያቸውም ነበር፡፡ ስለ ትውልድ አገራቸው ይመኩ ነበር፤ ስለዚህ ሌላ ልደት መስማት የሚኾንላቸው አይደለም፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ኒቆዲሞስን ‹‹ኒቆዲሞስ ሆይ፥ ስለ ምን በምስጢር በምሽት መጣህ? ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣ የእግዚአብሔር የሆነውንም ነገር እንደሚናገር እያወቅህ፡፡ ስለምን ከእርሱ ጋር ነገሮችን በግልጽ አልተወያየህም?›› ዓይነት ጥያቄዎችን አልጠየቀውም፡፡ አልወቀሰውምም፡፡ ነቢዩ እንዲህ ይላል፤ ‹‹አይጮኽም፤ ቃሉንም አያነሣም፡፡ ድምፁንም በሜዳ አያሰማም፡፡ የተቀጠቀጠ ሸምበቆን አይሰብርም፤ የሚጨስንም ክር አያጠፋም›› (ኢሳ. ፵፪፥፫)፡፡ ጌታ ራሱ እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ዓለሙን ላድን እንጂ በዓለሙ ልፈርድ አልመጣሁም›› (ዮሐ. ፲፪፥፵፯)፡፡

የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትሕትና ተመልከቱ! ‹‹እኔ ዂሉን በራሴ ማድረግ ይቻለኛልና የማንም ርዳታ አያስፈልገኝም፡፡ እኔ ራሴ እግዚአብሔር ነኝ፡፡ የያዝኩት ኀይል የአባቴን ኀይል ነው …›› አላለም፡፡ ይህንን ቢል ለሚያዳምጡት ወገኖች ቃሉን መቀበል ከባድ በኾነ ነበር፡፡

ነገር ግን ድርጊቱን ሲፈጽም በተመሳሳይ መንገድ አልነበረም፤ ምልክትን ሲያደርግ በኀይል ነው፤ ስለዚህም እንዲህ አለ፤ ‹‹ልትነጻ እወዳለሁ›› (ማቴ. ፰፥፫)፤ ‹‹ጣቢታ ተነሽ›› (ማር. ፭፥፬)፤ ‹‹እጅህን ዘርጋ›› (ማር. ፫፥፭) ‹‹ኀጢአትህ ተሰረየችልህ›› (ማቴ. ፱፥፪) ‹‹ፀጥ በል›› (ማር. ፬፥፴፱) ‹‹አልጋህን ተሸከምና ሒድ›› (ማቴ. ፱፥፮)፤ ‹‹አንተ ርኩስ መንፈስ ከዚህ ሰው ውጣ›› (ማር. ፭፥፰)፤ ‹‹ማንም ስለምን እንዲህ ታደርጋላችሁ ቢላችሁለጌታ ያስፈልገዋል› በሉት›› (ማር. ፲፩፥፫)፤ ‹‹ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትኾናለህ›› (ማር. ፳፫፥፵፫)፤ ‹‹ለቀደሙትአትግደል› እንደተባለ ሰምታችኋል፡፡ የገደለም ፍርድ ይገባዋል፡፡ እኔ ግን እላችኋለሁበወንድሙ ላይ የሚቆጣ ዂሉ ፍርድ ይገባዋል›› (ማቴ. ፭፥፳፩)፤ ‹‹ተከተለኝ፤ ሰውን አጥማጅ አደርግሃለሁ›› (ማቴ. ፩፥፲፯)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የጌታችንን አምላክነትና ትሕትና ሲያስረዳ እንዲህ ይላል፤ ‹‹ስለዚህ ነው ጌታ ኒቆዲሞስን በግልጥ ያናገረው፤ ነገር ግን የአብ የባሕርይ ልጅነቱን በመግለጽ አልጀመረም፤ ምልክት የሚያደርገው በተመሳሳይ ሥልጣን መኾኑን አልገለጠለትም፡፡›› 

በማንኛውም ኹኔታ የጌታችንን ታላቅ ሥልጣን እንመለከታለን፡፡ አምላካዊ ሥራን ሲሠራ ማንም ወገን በእርሱ ላይ ስሕተትን ማግኘት አይቻለውም፡፡ ነገር ግን ሊያጠምዱበት የሚቻላቸው በአንድ መንገድ ብቻ ነው እርሱም በንግግሩ ብቻ ነው፤ ማለት ንግግሩን በተሳሳተ መንገድ በመተርጐም፡፡ ኒቆዲሞስ በስሙ ከሚያምኑ ከጌታ ጋር ግን ግንኙነት ከሌላቸው ወገኖች አንዱ ነበረ፡፡ ስለዚህ በምሽት ወደ ጌታ ዘንድ መጣ፡፡ የመጣው ወደ ብርሃን ቢኾንም በጨለማ መጣ፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ የመጣው ወደ ጌታ ቢኾንም የመጣው በምሽትና የሚናገረው በጨለማ ነፍሱ ነበር፡፡ ስለዚህ በሰው ዂሉ ላይ የሚያበራውን ብርሃን የሚናገረውን መልእክት ሊረዳው አልተቻለውም፡፡

ኒቆዲሞስ መምህር ነበረ፡፡ ወደ እውነተኛው ብርሃን በጨለማ የመምጣቱ ምሥጢርም ምናልባት ለክብሩ ተጠንቅቆ ይኾናል፡፡ የሚያናግረውን ጌታ አምላክነት ገና አላወቀም ነበርና ፈራ፡፡ ኒቆዲሞስ በምሽት ወደ ጌታ የመጣው ለመጠመቅ አልነበረም፡፡ ለመማርና የጌታ ደቀ መዝሙርም ለመኾንም አይደለም፡፡ በአይሁድ ትውፊት መሠረት ማንም ወገን በምሽት ወደ አይሁድ እምነት፣ ለመገረዝ ወይም ለመጠመቅ አይመጣም፡፡ ይህ ሕግን መተላለፍ ነው፡፡ እንደ ተማሪ ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ ለመማር ሳይኾን የጌታን አሳብ ለማወቅና በጎዳናውም ይጓዝ ዘንድ ነው፡፡

የአይሁድ መምህር ‹‹ረቢ›› ብሎ ጌታን መጥራት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ የሕዝብ አለቃ ነኝ ብሎ የሚያስብ ሰው በትሕትና ረቢ ብሎ ሲናገር መመልከት በእርግጥም ያስደንቃል፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታን የጠየቀው ነፍሱ ስለምትድንበት ኹኔታ ብቻ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ስለ ጌታ አንድ ነገር ያውቃል፤ ጌታ በአይሁድ ምሁራን ወይም በታወቀ የአይሁድ ትምህርት ቤት ገብቶ የተማረ አይደለም፡፡ ትምህርቱ ከሰማይ ነው፡፡ ጌታ የያዘው የእውነትን ኀይል እንጂ የሰይፍን ኀይል አለመኾኑን ተገነዘበ፡፡ ከምድራዊው ጥበብ ባለፈ ፍጹም መለኮታዊ ጥበብ እንደሚናገርም ተገንዝቧል፡፡ የሚያደርገው ምልክት በመለኮታዊ ኀይል መኾኑን አስተውሏል፡፡

በጣም አስደናቂው ንግግሩ ደግሞ ‹‹መምህር ሆይከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን›› የሚለው ነው፡፡ ምናልባት ከእርሱ ጋር ሌሎች ሰዎች እንዳሉ ያመለክታል፤ ወይም ፈሪሳውያንን ወክሎ እየተናገረ ይኾናል፡፡ ምክንያቱም ምግባቸውም መጠጣቸውም ወሬአቸውም ክርስቶስ ኾኗልና፡፡ ከእነርሱ መካከል ኒቆዲሞስ የሚያምነውን እምነት የሚያምኑ ፈሪሳውያን ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ከእነርሱ መካከል ጌታን በግልጥ ወይም በስውር ሊያገኘው የፈለገ ወገን የለም፡፡

ይቆየን

ኒቆዲሞስ እና አዲሱ ልደት – የመጀመሪያ ክፍል

በዲ/ ታደለ ፈንታው

መጋቢት ፲፯ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት ብዙ አሕዛብ ወደ ክርስትና እምነት የተቀላቀሉበትን ምሥጢር የሚያስረዳ ምዕራፍ ነው፡፡ ድኅነትን በትጋት ለመፈጸም የሚታገሉ ክርስቲያኖች ይኼንን ምዕራፍ ሲያነቡ ከኒቆዲሞስ ጎን መቆማቸው የሚያጠራጥር አይኾንም፤ ከጌታ ጋር ምሥጢራዊ የኾነ ውይይትን መቀጠል ይፈልጋሉ፡፡ በሕይወታቸው የተከፈተ የአዲስ ኪዳን መንገድ እንዳለ ሲገነዘቡም ጌታን ይከተላሉ፡፡ ከእርሱ ጋር ከቅዱስ መንፈሱም ጋር አንድ ይኾናሉ፡፡ አዲስ ልደትን ያገኛሉ፤ ይህም በጥምቀት የሚገኝ የሥላሴ ልጅነት ነው፡፡

ይህ ምዕራፍ መልካም ሥነ ምግባር በነበረው ፈሪሳዊ ሕያውና መንፈሳዊ በኾነው ምንጭ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከል የነበረውን ውይይት ይዟል፡፡ ኒቆዲሞስ እንደ ፈሪሳዊ በአይሁድ ትውፊትና በብሉይ ኪዳን ትምህርት የታጠቀ ነው፡፡ ጠንካራ ሞራል እንደ ገነባ ሰው ወደ ጽድቅ የሚወስደውን ትውፊት የሚያውቅ ሰው በፈቃዱ መታዘዝ እንዳለበት የሚያምን ነው፡፡ ይህ የሚኾነው ደግሞ ሰው በሚያደርገው ጠንካራ ትግል እንደ ኾነ ያምናል፡፡ ይህ ትግል በሰው በጎ ፈቃድና ሕጉን በደረቁ በመተርጐም እንደሚገኝ ያምናል፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታን ያገኘው ሕጉን የሚቃወም ኾኖ ሳይኾን ሕጉን በጥልቀት የሚተረጕም አይሁዳዊ ኾኖ ነው፡፡ ስለዚህም ነው ወደ መድኀኒታችን ከተሳቡ ወገኖች መካከል ወንጌላዊው የኒቆዲሞስን ጉዳይ በትኩረት የጻፈው፡፡

ወንጌላዊው እንደ ነገረን ኒቆዲሞስ ጌታ ከእግዚአብሔር እንደ መጣ አወቀ፤ አመነም (ዮሐ. ፫፥፪)፡፡ ነገር ግን ምናልባት ኒቆዲሞስ ጌታ ትምህርቱን ማኅበራዊ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚያስተምር ሊያስብ ይችላል፡፡ የሕጉን ጥሬ ትርጕም እንጂ ፍካሬያዊ ትርጕም አልተገነዘበም፡፡ የአይሁድን ኑሮ ሊያሻሽል የመጣ ነው ብሎም ሊያስብ ይችላል፡፡ የኒቆዲሞስ አመለካከቱና ልምዱ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለውን አዲስ ሕይወት ለመቀበል አያበቃውም፡፡ በአዲሱ ልደት የሚገኘው የጸጋ ልጅነት አይገነዘበውም፡፡ የመንፈሳዊው ሕግ ጥቅም ግን ይህ ነበር፡፡ ሥጋዊውን ከመንፈሳዊ ምድራዊውን ከሰማያዊ መለየት ያስችላል፡፡ ጌታ የኒቆዲሞስን አሳቡን፣ ልቡን፣ ስሜቱን፣ ዕውቀቱን ዂሉ ወደ ሰማያዊ ነገር እንዲያሸጋግረው ፈቀደ፡፡ ይህን በማድረግ ከሰማይ የወረደው እርሱም በሰማይ የነበረው እንደ ኾነ ይገነዘባል፡፡ ወደ ሰማይ መውጣትም የሚቻለው እርሱ ነው፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ወገኖችን ከፍ ከፍ የሚያደርጋቸው፤ ከፍ ያለውንም ነገር እንዲመለከቱ የሚያደርጋቸው እርሱ ነው፡፡

የኒቆዲሞስና የጌታ ግንኙነት ትኩረታችንን ወደ ክርስቶስ እንድናደርግ ያደርገናል፡፡ ለእያንዳንዱ የሰው ልጅ ነፍስ መዳን ምን ያህል ትኩረት እንደሚሰጥ ከእያንዳንዱም ወገን ጋር ሲነጋገር ያለውን ትሕትናም እንገነዘባለን፡፡ ከኒቆዲሞስ ጋር ሲወያይ የአዲሱን ልደት ጠባይ ዘርዝሯል፡፡ ኒቆዲሞስ የእግዚአብሔርን መንግሥት ማወቅ ፈልጓል፤ ይኼንን መንግሥት ለማወቅ በውኃና በመንፈስ ይጠመቅ ዘንድ ግድ መኾኑን ያስረዳል፡፡ ይህ ኹኔታ አስፈላጊ ነው፤ ክርስቲያን ዘወትር የእግዚአብሔር ልጅ ኾኖ እንዲኖር ያስችለዋልና ይጠመቅ ዘንድ የግድ ነው፤ በመንፈሱም እንዲኖር ያደርገዋል፡፡ በዚህ ምዕራፍ ጌታ ከምድራዊ ነገሮች ያወጣና አሳባችን ሰማያዊ በኾነው ጉዳይ እንዲያዝ ያደርጋል፡፡ ይህንን ማድረግ የምንችለው ከሰማያዊው ጋር ኅብረት ስንፈጥር መኾኑን ይነግረናል፡፡

ጌታ ጥምቀቱን ከመስቀሉ ጋር አያይዞታል፡፡ እግዚአብሔር አብ ለሰው ልጆች ዂሉ ያለውን እውነተኛ ፍቅር የገለጠበት፣ የባሕርይ ልጁን ወደ ዓለም በመላክ ዓለሙ ዘላለማዊ ሕይወትን ያገኝ ዘንድ ልጁ ከፍ ከፍ ያለበትም የነገሠበትም ዙፋኑ ነውና፡፡ አዲሱን ልደትን በማንሣት ጌታ ከፍርሃት ባርነት አውጥቶ መለኮታዊ የኾነውን ብርሃን እንድንመለከት ያደርገናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ጌታ ሲጠመቅ የነበረውን ኹኔታ ሲነግረን ለሚያምኑ ወገኖች ያለውን አንድምታም ሲገልጽ ደስታው ፍጹም ነበር፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስ በወንጌሉ ከሰጠው ትምህርት መካከል ከምዕራፍ ፩ – ፫ ስለ አዲሱ ልደት ማብራሪያ ይሰጣል፡፡

ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የኾነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንደ ሰው ነበረ፡፡ ‹ኒቆዲሞስ› የአይሁድ ስም ሲኾን ትርጓሜው ‹ሕዝብን ያሸነፈ› ማለት ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ አካል የሰንሃድሪን አይሁድ ሸንጎም አባል ነው፡፡ የክርስቶስ መለኮታዊ ጥሪ መላውን የሰው ልጆች ያካተተ ነው፡፡ የመደብ ልዩነት አልተደረገበትም፡፡ ነገር ግን በከፍተኛ ሓላፊነት ከነበሩ የመንግሥትና የሃይማኖት መሪዎች መካከል ለዚህ ጥሪ መልስ የሰጡ ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ከፈሪሳውያን መካከል እጅግ ጥቂቶች፤ ከጥቂቶቹ አንዱ ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ በአይሁድ ሸንጎ የተከበረ ሰው ነበረ፡፡ ጌታ ግን ይህችን አንዲት ለመዳን የወሰነች ነፍስ ዝቅ አላደረጋትም፤ ሞትን የተቀበለው ስለእያንዳንዱ ነፍስ ነውና፡፡

ፈሪሳውያን ለመለኮታዊው እውነት የሰጡት መልስ ጥላቻና የዐመፅ መንፈስን የተመላ ነው፡፡ ነገር ግን ከተማሩ አይሁድ መካከል ጌታን ለማግኘት የቸኮሉ በሩም ተከፍቶ የጠበቃቸው ጥቂቶች ነበሩ፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋ በተማሩም ባልተማሩም ወገኖች ላይ ይሠራል፡፡ በተራውም ሕዝብ፣ በአለቃውም፣ በየዋሁም፣ በዐመፀኛውም ላይ ይሠራል፡፡ ኒቆዲሞስ ደረጃው ከዐመፀኞቹ ቢኾንም ወደ ጌታ መጣ፤ ጊዜው ሲደርስ የቻለውን ያህል ይጠይቅና ያውቅ ዘንድ ሞከረ፡፡ በጥያቄ ላይ እንደ ነበረ ታሪኩ ያስረዳል፡፡ ጊዜው ሲደርስ ለደቀ መዛሙርቱ ያልተቻለው ለዚህ ሰው ተቻለ፡፡ ከጲላጦስ አስፈቀዶ አዲስ ባሳነጸው መቃብር ላይ እንዲቀበር አደረገ፡፡

ቤን ረጊን በአይሁድ ታሪክ መጽሐፍ ስለ ኒቆዲሞስ ሲናገር ይህ ሰው በጣም ሀብታም ከመሆኑ የተነሣ በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙዎችን ለብዙ ዓመታት ይረዳ እንደ ነበር ይናገራል፡፡ እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ ‹‹መምህር ሆይ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከኾነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለም፡፡ መምህርነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን›› አለው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ኒቆዲሞስን በብዙ ቦታዎች ጠርቶታል፡፡ ጌታን ማታ ማታ ይጐበኝ እንደ ነበረም ገልጧል፤ ይህ ኹኔታ ሦስት ጊዜ ያህል ተጠቅሷል (ዮሐ. ፫፥፪፤ ፱፥፴፱፤ ፯፥፶)፡፡

ኒቆዲሞስ ስለ ምን ወደ ጌታ በምሽት መጣ

የመጀመሪያው ምክንያት ጌታችን በአደባባይ የሚያስተምረውን ትምህርት ከሰዎች መስማቱ ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ ከምንም በላይ ጌታ በአደባባይ የሚያደርገውን ምልክት በሕዝብ መካከል በግልጽ መጥቶ ማየት አልወደደም፡፡ ድኅነትና ነፍስን የሚመለከቱ ጉዳዮችን በጥሞና ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ መነጋገር ልቡ ፈቅዷል፡፡ ‹‹ቃሌስ በቅንነት ለሚሔድ በጎ አያደርግምን?›› (ሚክ. ፪፥፯) ተብሎ እንደ ተጻፈ ኒቆዲሞስ የቅንነትን መንገድ መርጦ ወደ ጌታ ቀርቧል፡፡ ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ይነጋገር ዘንድ ወደደ፡፡ ጌታ እንኳን ከሕዝቡና ከደቀ መዛሙርቱ ተለይቶ ከአብ ጋር ሲነጋገር የሚያድርበት ጊዜ ነበር፡፡ እኛማ ሌሊቱን በሙሉ ከእግዚአብሔር ጋር እንደምን መነጋገር ይገባን ይኾን? በተለይ በሌሊት ዂሉንም ነገር ትተን ከጌታ ጋር መገናኘት ይጠበቅብናል፡፡ አዲሱን ሕይወትና የዚህን ሕይወት ባሕርይ፣ በዚህ ሕይወትም ውስጥ ካለች ከመንፈስ ኅብረት ተካፋዮች እንኾን ዘንድ ይገባናል፡፡

ሁለተኛው ምክንያት ምናልባት ጥበብን ለመማር የማታው ጊዜ የተሻለ እንደ ኾነ በመረዳቱ ነው፡፡ ጌታ ቀን ቀን ሕዝቡን ሲያስተምር እንደሚውል ያውቃል፡፡ ስለዚህም ኒቆዲሞስ ጌታን በምሽት ጠብቆ ለማግኘትና ለማግኘትና የድኅነትን ትምህርት ለመማር ወደደ፡፡

ሦስተኛው ምክንያት አንዳንድ ምልክቶችን ከተመለከተ በኋላ ጌታን ለማግኘት የመጀመሪያውን ዕድል በምሽት ማግኘቱ ነው፡፡ ዂሉም ሰው ሲተኛ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መንፈሳዊ ምሽትን ማሳለፍ ፈልጓል፡፡ ምናልባትም እንዲህ ዓይነት ዕድል ወደፊት ሊገጥመው እንደማይችል ሥጋት አድሮበት ሊኾን ይችላል፡፡

አራተኛው እንደ ነቢዩ ዳዊት ምሳሌውን ሊከተል ፈልጎ ነው፡፡ ዳዊት ሌሊቱን ለምስጋና ይጠቀምበት ነበርና (መዝ. ፴፮፥፮፤ ፻፲፱፥፻፵፰)፡፡

ይቆየን

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – የመጨረሻ ክፍል

የካቲት ፴ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፬. ነገረ ማርያም

፬.፩ አንጢዲቆማርያጦስ

እነዚህ መናፍቃን “አፅራረ ማርያም (የማርያም ጠላቶች)” ይባላሉ፡፡ መድኃኒታችንን ከወለደች በኋላ ከዮሴፍ ጋር በባልና ሚስት ልማድ ኖረች በማለት በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ላይ የጽርፈት ቃል የሚናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ለኑፋቄያቸው መነሻ ያደረጉት የበኵር ልጇን እስከምትወልድ ድረስ አላወቃትም የሚለው ንባብ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም ይህ ንባብ እንዴት እንደሚፈታና እንዴት እንደሚተረጎም በማመሥጠር ለእነዚህ ዝንጉዓን መልስ ይሰጣቸዋል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሕና፣ ቅድስናና ዘለዓለማዊ ድንግልና ቅዱሳት መጻሕፍትን በመጥቀስ ከተከራከራቸው በኋላ የመለኮትን አዳራሽ ሊቀርባት የሚችል የትኛው ሥጋዊ ነው? ምን ሰው ወደ መለኮት አዳራሽ ሊገባ ይችላል? በማለት ያሳፍራቸዋል፡፡ እኛ ግንድንግል ማርያምን የአምላክ እናት ናት፤ ከወለደችውም በኋላ ዘለዓለማዊት ድንግል ናት› እንላለን ይላል፡፡

፬.፪ “እመቤታችን በሩካቤ አልተወለደችም” ለሚሉ

አባ ጊዮርጊስ ለእነዚህ መናፍቃን መልስ ሲሰጥ “… መልአኩእነሆ ትፀንሻለሽ፤ ወልድንም ትወልጃለሽብሎ የምሥራች በነገራት ጊዜወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆንልኛል?› ብላ ያደነቀች እርሷን እንደምንበሩካቤ አልተወለደችምይሏታል? እናቷ እርሷን ያለ ሩካቤ ፀንሳት ቢሆን ኖሮ ድንግልወንድ ስለማላውቅ ይህ እንደምን ሆንልኛል?› ባላለች ነበር! በማለት አባቷ ኢያቄም እናቷም ሐና መሆኗን በመጥቀስ ያሳፍራቸዋል፡፡

፬.፫ ድንግል ማርያምና መስቀልን ለሚያበላልጡ

ሊቁ እነዚህን ስለ ማርያምና ስለመስቀል እንደሚክዱ በጆሯችን የገባ ወሬ አለ፡፡ እኩሌቶቹ የወለደችው ማርያም ከመስቀሉ ትበልጣለች ይላሉ፤ እኩሌቶቹም በሕማማቱ ደም የተቀደሰ መስቀል ይበልጣል ይላሉ፡፡ እኛ ግን ማርያም አምላክን የወለደች እንደሆነች እናምናለን፡፡ መስቀሉም መለኮት በተዋሐደው የትስብእት ደም የተቀደሰ የብርሃን ማዕተብ መሆኑን እናምናለን በማለት ይመልስላቸዋል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ከእነዚህም በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለማጣመም ለሚሞክሩ ሌሎች ስሑታንም መልስ ሰጥቷል፡፡ የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያህል፡-

  • “ወደ ቤተ ክርስቲያን ኃይል አይወርድም፣ ኅብስቱም ወደ ክርስቶስ ሥጋነት፣ ወይኑም ደሙን ወደ መሆን አይለወጥም ለሚሉ ሊቁ ሲመልስ “‹ሰማየ ሰማያት የማይወስነው እግዚአብሔር አራት ጎኖቿ ባነሱ በሰው እጅ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዴት ያድራል?› የሚሉ አሉ፡፡ እኛ ግንበጽርሐ አርያም ያለ አኗኗሩ ሳይጎድል ይቀድሳት ዘንድ የመለኮት ኃይል በቤተ ክርስቲያን ያድራል› እንላለንይላል፡፡ በተጨማሪም “… ከከሐዲዎች መነሣሣት የተነሣ እንዳትነዋወጥ ኃይል ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቃታል፡፡ የሚጠብቃት እርሱ ሲሆን ኃይልን ትሸከመዋለች፤ ኃይል ትጎናጸፋለች፤ ኃይልም ትታጠቃለች፤ ኃይላትም ይከቧታል፤ የሠራዊት ጌታ ሠረገላ አድርጓታልና በማለት ይመልስላቸዋል፡፡
  • ስለ ሥጋ ወደሙም “‹ኅብስቱ የክርስቶስን ሥጋ፣ ወይኑም ደሙን መሆን ይችላልን?የሚሉ አሉ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ በተቀደሰ ጊዜ ኅብስት ከልማዳዊ ኅብስትነት ሥጋውን ወደ መሆን ይለወጣል፤ ወይንም ከልማዳዊ ወይንነት ደሙን ወደ መሆን ይለወጣል በማለት ምሥጢረ ቍርባንን ያብራራል፡፡ ለድንግል የእግዚአብሔር ልጅ በመንፈስ ቅዱስ መምጣት ልጅ ሆናት፤ እርሷም በልዑል ኃይል እናት ሆነችው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ወደ እርሷ ባይመጣ፣ የልዑል ኃይልም ባይጋርዳት የልዑልን ልጅ ትሸከመው ዘንድ ባልተቻላት ነበር፡፡ ኅብስቱና ወይኑም እንዲሁ ካህኑ አቤቱ የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋና ደም እንዲያደርገውበዚህ ኅብስትና ጽዋ ላይ ቅዱሱን ኃይል ትልክ ዘንድ እንለምንሃለን፤ እንማልድሃለንባለ ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ መውረድ ሥጋና ደም ይሆናል በማለት ይመልሳል፡፡
  • ስለ ምሥጢረ ሥጋዌም የሚከተለውን ትምህርት ያስተምራል፤በማርያም ማኅፀን ፍጹም የሕይወት እንጀራ ተፀነሰ፡፡ ይኸውም ለተቀደሰች ምሥጢር የበረከት ፍሬ ሆኖ የተሰጠ ከአብርሃም ዘር የተገኘ ሥጋ ነው፡፡ ከባሕርይዋ ደምም በመንፈስ ቅዱስ መጐብኘት የወይን ፍሬ አፈራ፡፡ በአብም በመጋረዱ ኃይል የሚናገር የወይን ደም የመለኮትም ሥጋ ኅብስት ተፀነሰ፡፡ ስለዚህም መድኃኒታችንከሰማያት የወረደ የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ሥጋዬን የበላ የእኔን ሥጋ ስለበላ በሕይወት ይኖራል፤ ደሜንም የጠጣ ሞትን አይቀምስም› አለ፡፡ ዳግመኛምአብ ሕያው እንደሆነ እኔም የአብ ልጅ ስለሆንሁ ሕያው ነኝሥጋዬንም የበላ የእኔን ሥጋ ስለበላ በሕይወት ይኖራል› አለ፡፡ እንዲህ ያለውን ጸጋ አቃልለን እንደምን እንድናለን? እኛ ግን በመንበሩ ላይ ሆኖ በካህኑ እጆች የሚከብረው ኅብስትና ወይኑ ፍጹም የክርስቶስ ሥጋና ደም እንደሆነ እናምናለን፡፡

፬.፬ ሰዱቃውያን

ሰዱቃውያን ትንሣኤ ሙታን የለም የሚሉ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ ጌታችን በሥጋዌው ወራት በትንሣኤስ እንደ እግዚአብሔር መላእክት በሰማይ ይሆናሉ እንጂ አያገቡም አይጋቡምም በማለት የመለሰላቸውን እየጠቀሰ መልስ ይሰጣቸዋል (ማቴ. ፳፪፡፴)፡፡

  • ነፍስ ከሥጋ ጋር ትሞታለች” ለሚለው፡- ይህ መናፍቅ ነፍስ ከሥጋ ጋር ትሞታለች፤ ሙታን በተነሡ ጊዜ ከሥጋ ጋር ትነሣለች የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ሊቁም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴዎስ ወንጌል ላይ ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ በማለት የተናገረውን በመጥቀስ ነፍስ የማትሞት መሆኗን ይመልስለታል (ማቴ. ፲፡፳፰)፡፡ ነፍስ ከሥጋ ተለይታ በሲኦል ወይም በገነት እንደምትቆይ የአልዓዛርን ታሪክ ድሀውም ሞተ፤ መላእክትም ወደ አብርሃም እቅፍ ወሰዱት የሚለውን በመጥቀስ ያሳፍረዋል (ሉቃ. ፲፮፡፳፪)፡፡
  • “… በዐርባ ቀን እግዚአብሔር በሕፃኑ ፊት ላይ የሕይወትን እስትንፋስ እፍ ይልበታል፤ በእግዚአብሔርም እጅ ይፈጠራልበማለት የተሳሳተ ትምህርት ለሚያስተምሩ ዝንጉዓን፡ ሊቁ እግዚአብሔር የሕይወት እስትንፋስን በአዳም ላይ እፍ እንዳለ በሔዋን ፊት ላይ ግን የሕይወትን እስትንፋስ እፍ እንዳላለ እይ፤ ሕፃን ከእግዚአብሔር አፍ የሕይወትን እስትንፋስ መቀበል የሚገባው ቢሆን ሔዋን ከፈጣሪዋ ከእግዚአብሔር አፍ ዳግመኛ የሕይወትን አስትንፋስ መቀበል በተገባት ነበር በማለት ትክክለኛው የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ሕፃን ልጅ ከአባቱና ከእናቱ ዘር የማትሞት ነፍስን ይቀበላል የሚለው እንደሆነ ገለጸልን፡፡
  • “ኦሪት፣ ነቢያትና ሰንበት ተሽረዋልለሚሉ፡- በወንጌል መምጣት ኦሪት እንደ ቀረች፣ በሐዋርያትም ስብከት የነቢያት ትንቢት እንደጠፋ፣ ሰንበትም ትንሣኤ በሆነባት እሑድ እንደተሻረች የሚናገሩ አሉ፡፡ እኛ ግንኦሪት በወንጌል ስብከት ከበረች፤ ነቢያትም በሐዋርያት ትምህርት ከፍ ክፍ አሉ፤ ዓለምን ከመፍጠር ያረፈባት ሰንበትም የዓለም አዳኝ በተነሣባት በሰንበተ ክርስቲያን ዘውድን ተቀዳጀች› እንላለንበማለት ይመልስላቸዋል፡፡
  • አዳምና ነቢያት በሲኦል አልነበሩም ለሚሉ፡- አባ ጊዮርጊስ እንዲህ የሚሉትን መናፍቃን ነቢያት የተናገሩትን በመጥቀስ እስከ ክርስቶስ መምጣት ድረስ በሲኦል ስለመኖራቸው፣ ገነትም ተዘግታ በምትገለባበጥ የእሳት ሰይፍ እየተጠበቀች መቆየቷን በመግለጽ ይገሥጻቸዋል፡፡
  • “ኤዶም ገነትና ሲኦል በሰማያት ናቸው” ለሚሉ፡- የተወሰኑት ኤዶም ገነት በሰማያት ናት፤ በምድር አይደለችም” ሲሉ፤ ሌሎቹ ደግሞ ሲኦል በሰማያት ናት” ይላሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ገነትና ሲኦል ቁጥራቸው ከዓለመ ምድር እንጂ ከሰማያት እንዳልሆኑ ገነትን የሚያጠጡ ወንዞችን፣ አዳም ወደ ገነት እንዳይገባ በሱራፊ መጠበቋን ከቅዱሳት መጻሕፍት እየጠቀሰ መልስ ሰጥቷቸዋል፡፡

በአጠቃላይ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በመጽሐፈ ምሥጢር መጽሐፉ የመናፍቃንን ስሕተትና የስሕተታቸውን ምክንያት ነቅሶ በማውጣትና መጽሐፋዊ የሆነ መልስ በመስጠት መናፍቃንንና ስሑታንን ገሥጿል፡፡ የመጽሐፉ ዋና ትኩረት ምሥጢረ ሥላሴና ምሥጢረ ሥጋዌ ላይ ለተነሡ ኑፋቄዎች መልስ መስጠት ቢሆንም ሌሎችንም ጉዳዮች በማንሣት መልስ እንደ ሰጠ ከላይ ተመልክተናል፡፡ አዲስ መናፍቅ እንጂ አዲስ ኑፋቄ የለም እንደሚባለው በመጽሐፉ የተጠቀሱ መናፍቃን ትምህርቶች ዛሬም ድረስ በተለያዩ አካላት እንደ አዲስ ሲጠቀሱና ሲነገሩ እንሰማለን፡፡ በዘመናችን የተነሡ መናፍቃንና ግብረ አበሮቻቸው የሚያስተምሩትም ቤተ ክርስቲያን አውግዛ የለየችውና በየዘመናቱ የተነሡ ሊቃውንት መልስ የሰጡበት እንጂ አዲስ የተገለጠላቸው ትምህርት አለመሆኑን መረዳት ከክርስቲያኖች ይጠበቃል፡፡ ትምህርቷን ያልሰሙ አላዋቂዎች ዛሬም ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስን እንደማትሰብክ አድርገው ይናገራሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስን እንዴት እንደምትሰብከው በሚያስረዳው በሚከተለው የሊቁ ቃል ጽሑፋችንን እናጠቃልላን፤

ኢየሱስ ክርስቶስ የቅዱሳን ሁሉ ንጉሥ ነው፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚጠራው ስሙ የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚያዳምጠው ቃሉ የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚበላው ሥጋው የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚጠጣው ደሙ የጣፈጠ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ዜናውን ለሚነግር መታሰቢያው የጣፈጠ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ የሰውም ልጅ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል ያለ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ እትራቶቹ ከእርሱ ጋር መስቀሉም በፊቱ ያለ፣ የአንድነታችን አለቃ፣ የትምህርታችን አስተማሪ፣ የእረኞቻችን አለቃ፣ የካህኖቻችን ሊቅ ነው፡፡ እርሱ ሰማያዊ ከሚሆን ከቸር አባቱና ሕይወትን ከሚሰጥ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እስከ ዘለዓለሙ ድረስ ከእኛ ጋር ይኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳም ድረ ገጽ ተከታታዮች! ይህ ትምህርት፣ ከጥር ፩ – ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በታተመው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በንቁ ዓምድ ሥር ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – ሦስተኛ ክፍል

የካቲት ፳፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፪.፬ አርአያውን ወደ መስቀል አወጣ ለሚሉ መናፍቃን

ሥጋው የተቸነከረው በእውነት ካልሆነ ስለምን ከትንሣኤው በኋላ ቶማስንእጅህን አምጣና በመስቀል ችንካሮች የተጨነከሩትን እጆቼን ዳስስ፤ ጣቶችህንም አምጣወደ ጎኔም አስገባአለው በማለት ሊቁ ስንፍናቸውን ይገልጽባቸዋል፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዞ አባ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አይወልድም አይወለድም ለሚሉ መናፍቃን እነዚህን በምን እንከራከራቸዋለን፤የኦሪት ሕግ አለንይሉናል፡፡ የኦሪታቸው ቃል ከእኛ ኦሪት ጋር፣ የነቢዮቻቸውም ቃል ከእኛ ነቢያት ጋር አይተባበርምና የአንደበታቸው ቃል ሁሉ ሐሰተኛ ነው፤ መንገዳቸውም ክፉ መንገድ ነው …” በማለት ክሕደታቸውን ይገልጽልናል፡፡

፪.፭ አርሲስ

“አርሲስ” በሃይማኖተ አበው እንደተጠቀሰው ስመ መናፍቃን ነው፡፡ አርሲስ በነፍስና በሥጋ ወደ ሲኦል ወረደ ብለው የሚናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ እነዚህን መናፍቃን እስኪ እናንተ አስቀድማችሁ ንገሩን? የእግዚአብሔርን ልጅሞተ› ትሉታላችሁ? ወይስአልሞተምትላላችሁ?ብሎ ይጠይቃቸዋል፡፡ ሞተ” ካሉ “የነፍስ ከሥጋ መለየት በቀር ሞት ምንድን ነው?” አልሞተም” ካሉ ደግሞ ሞት ሳይኖር ትንሣኤ እንዴት ነው?” እያለ ይሞግታቸዋል፡፡ በትምህርታቸው ክርስቶስን የሚሞትና የማይሞት ሁለት ሥጋ ያለው እንዳስመሰሉት በመንገር ይነቅፋቸዋል፡፡ እኛ ግንመለኮታዊ ቃል ከብቻዋ ከነፍስ ጋር ወደ ሲኦል ወረደ፤ ሥጋን ግን ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከመስቀል ላይ አውርደዋት በከፈን ጠቅልለው ከመቃብር ውስጥ ጨመሯት፡፡ ሥጋም ያለ ነፍስ እስከ ትንሣኤው ዕለት ለብቻዋ ቆየች፡፡ መለኮት ግን ከነፍሱ እና ከሥጋው አልተለየም› እንላለን” በማለት መልስ ያሰጣቸዋል፡፡

፪.፮ ፎጢኖስ

በሰርቢያ ግዛት ትገኝ በነበረች የሰርሚየም ሊቀ ጳጳስ የነበረው ፎጢኖስ ለፌ እማርያም ክዋኔሁ (ህላዌሁ) ለወልድየወልድ ህልውና ከማርያም ከተወለደ በኋላ ነው የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስም እኛ ግንህልውናው ከዘመናትና ከጊዜ፣ ከዕለታትና ከሰዓት አስቀድሞ ነው፣ በኋለኛው ዘመን ስለ እኛ ድኅነት ያለ ዘርዐ ብእሲ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሰው ሆነ (በሥጋ ተገለጠ)› እንላለን በማለት ቅዱሳት መጻሕፍትን እያመሠጠረ መልስ ሰጥቶታል፡፡

፪.፯ የአብ ቃል ሰው ወደመሆን ተለወጠ ለሚሉ መናፍቃን

እነዚህ መናፍቃን አካላዊ ቃል ሥጋና ደም፣ አጥንትና ጠጉር፣ ሥሮችንም ወደ መሆን ተለወጠ፤ መለኮትም ሰውን ወደ መሆን ተለወጠ ብለው ይናገራሉ፡፡ ይህም ማለት ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የሆነው ተለውጦ ነው ወይም ሰው በመሆኑ አምላክነቱ ጠፍቷል” የሚሉ ናቸው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን ሰው ሆነ ሲባል የጨው ሐውልት እንደሆነች እንደ ሎጥ ሚስት፣ የበርሃ አውሬ እንደሆነ እንደ ናቡከደነፆር ተለውጦ አይደለም ይላል፡፡ የመለኮት ኃይል ሰው ወደ መሆን ተለውጦ ቢሆን ኖሮ ሞትን ባልቀመሰ፣ ሞትንም ቢቀምስ ዓለምን የያዘው የመለኮት ኃይል ነውና፣ የሰማይ ጠፈር በፈረሰ፣ የምድርም መሠረታት በተበታተኑ ነበር፤ ሰውነት መለኮትን ወደ መሆን ተለውጦ ቢሆን መለኮት በእጅ አይነካም፣ ለዐይንም አይታይም፣ በሕሊናም አይመረመርምና ለሰቃዮች ባልተያዘ፣ በመስቀል ላይ እፍረትን ባልታገሠ ነበር በማለት ይዘልፋቸዋል፡፡ እኛ ግንያለጭማሪ ተዋሐደ እንጂ መለኮታዊ ቃል ከባሕርዩ አልተለወጠም፤ ያለመለወጥ የተዋሐደ ሆነእንላለን በማለት በተዐቅቦ እንደተገለጠ ይነግረናል፡፡

፪.፰ መንክዮስ

የክርስቶስ ሥጋ ምትሐት ነው፤ የሰው ልጅ ሥጋ አይደለም የሚል ኑፋቄ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ የክርስቶስ ሥጋ ምትሐት አለመሆኑን፣ ፍጹም የሰው ሥጋ መሆኑን ከድንግል መወለዱን፣ ጡቶቿን እየጠባ ማደጉን፣ በዮርዳኖስ በዮሐንስ እጅ መዳሰሱን፣ በመስቀል ላይ መቸንከሩን በመጥቀስ መንክዮስ ሆይ! ስንፍናህን አደንቃለሁስለ ብዙዎች ቤዛ መገደሉን ካላመንክ አንተም በኢየሱስ ክርስቶስ ሞት አልዳንህም በማለት ይዘልፈዋል፡፡ እኛ ግን የክርስቶስ ሰውነት ፍጹም የሚዳሰስ ሥጋን የሚያጸና አጥንት የሚፈስ ደም ሰውነትንን የሚያስሩ ጅማቶች፣ የራስ ጠጉርና ቅንድብ፣ የማትታይ ነፍስ የምታስተውልና የምትናገር የሕይወት እስትንፋስ፣ የእጆችና የእግሮች ቡቃያ ጥፍሮች አሉት እንላለን ይለናል፡፡

፪.፱ አውጣኪ

አውጣኪ ወይም አፍቲኪስ የክርስቶስ ሥጋ እንደኛ ሥጋ አይደለም፤ መከራንም አልተቀበለም፤ የክርስቶስ ሥጋ ከሰማይ የወረደ ነው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አውጣኪ ነገረ ተዋሕዶን ለማብራራት ሲሞክር ኢየሱስ ክርስቶስ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ ነው” የሚለውን ትምህርት ቢቀበልም፣ በሥጋው ፍጹም ሰው መሆኑን ግን አልተቀበለም፡፡ ስለዚህ ክርስቶስ ተራበ፤ ተጠማ፤ ደከመ፤ መከራ ተቀበለ፤ ሞተ …” የሚሉትን ቃላት ለመጠቀም ይፈራል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወደ ደረቱ ተጠግቶ የተቀመጠ ወዳጁ ዮሐንስ የክርስቶስን ሥጋ መድከም ለመናገር ካላፈረ፣ በፊቱ መስታወትነት ያልታየህ፣ ጣቶቹ ያልዳሰሱህ፣ ጣቶችህም ያልዳሰሱት አንተ እንዴት ታፍርበታልህ? በማለት የሚወቅሰው ስለዚህ ነው፡፡ እኛ ግን ክርስቶስ በሥጋው ደከመ፣ ወዛ፣ ተራበ፣ ተጠማ፣ ታመመ፣ ሞተ፤ ከኃጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ ሁሉ ሠራ እንላለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ቀጥተኛ አስተምህሮ በመግለጥ እኛን ስለማዳን ከተያዘበት ጊዜ ጀምሮ ቅድስት ነፍሱ ከቅዱስ ሥጋው እስከተለየችበት ድረስ የተቀበለውን ፀዋትወ መከራ ያብራራል፡፡

በተጨማሪም አፍቲኪስ የክርስቶስ ሥጋ ከሰማይ ወረደ በማለት ለሚናገረው ኑፋቄው ሊቁ ሲመልስ እናንተ ሰነፎችና ልባችሁ ከማመን የዘገየአዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ› ብሎ መናገርን እንዳስቀደመ ከአዳም ዘር ሰው ሆኖ እንደተወለደ ዕወቁ፡፡ መድኃኒታችን ከለበሰው ከአዳም ሥጋ በቀር የአዳም እንደ እግዚአብሔር መሆኑ ምንድን ነው? በዚያችም ሥጋ በምድር ላይ ጉስቁልናን ለበሰ፤ ያችንም ሥጋ በሰማያት ጌትነትን አለበሳት፡፡ በሰማያት ሥጋ ካለ ከእርሷ ሰው ሆኖ ይወለድ ዘንድ ስለምን በድንግል ማኅፀን አደረ፣ ከሥጋው ጋር በድንግል ማኅፀን አደረ ካላችሁ፣ የሥጋ በሥጋ ውስጥ ማደር ጥቅሙ ምንድን ነው? ቀድሞውንም ሥጋ ካለው የቀደመ ሥጋው በበቃው፤ ከድንግል ሥጋ መወለድን ባልፈለገ ነበር ይላል፡፡ እኛ ግንየክርስቶስ ሥጋና ነፍሱ ከአዳም ባሕርይ ብቻዋን ንጽሕት ድንግል (ከሆነች) ማርያም ከተባለች የገሊላ ሴት ያለ ወንድ ዘር የነሣው ነው› እንላለን በማለት ይመልስለታል፡፡

አባ ጊዮርጊስ የክርስቶስን አምላክነት በመሰከረበት በዚህ አንቀጹ የሚከተለውን ትምህርት አስተምሯል፤ ስለ ትሕትና ነገር መናገርን እናስቀድም፤ ኃይል በሴት ማኅፀን አደረ፤ እሳትም በሥጋና በደም መጐናጸፊያ ተጠቀለለ፡፡ ሕፃናትንም የሚሥል በሕፃናት መልክ ተሣለ፤ የሔዋን አባት ከሔዋን ሴት ልጅ ተወለደ፤ በኪሩቤል ላይ የሚቀመጥ በጉልበት ታቀፈ፤ እሳት በተሣለባቸው በአራቱ እንሰሳ ላይ የሚጫን በላምና በአህያ መካከል ተኛ፡፡ ሥጋዊን ሁሉ የሚመግበው የጡት ወተትን ተመገበ፡፡ በጊዜና በዘመናት የሸመገለ በየጥቂቱ አደገ፤ በታናሽነታቸው ጊዜ ሕፃናትን የሚጠብቃቸው በሜዳ ላይ ዳኸ፤ ለዓመታቱ ቁጥር ጥንት የሌለው በሰው መጠን ጐለመሰ፤ ተራሮችን በኃይል የሚያቆማቸው ደከመ፣ ወዛም፡፡ ኪሩቤል ሊነኩት ሱራፌልም ሊዳስሱት የማይቻላቸው እግሮቹ በአመንዝራይቱ ሴት፣ ልብሶቹም ደም በሚፈስሳት ሴት ተዳሰሰ፡፡

፪.፲ የእለእስክንድርያው ታውዶስዮስና የሕንድክያው ሳዊሮስ

እነዚህ የእግዚአብሔር ልጅ በግድ መከራን ተቀበለ፤ ያለፈቃዱ ሞተ ብለው የተናገሩ መናፍቃን ናቸው፡፡ ሊቁ ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት” ማለቱን፣ አትሙትብን” ያለውን ቅዱስ ጴጥሮስን መገሠጹን፣ ነፍሴን ላኖራት ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ” ማለቱን እየጠቀሰ ካሳፈራቸው በኋላ እኛ ግን በፈቃዱ መከራ ተቀብሎ ሞተ፣ በፈቃዱ በመለኮቱ ኃይል ተነሣ እንላለን ይላል፡፡ በፈቃዱ ስለሆነ መከራውና ሞቱም እርሱ ራሱ በፈቀደ አሰቃዩት፤ እርሱም በወደደ ገደሉት፤ እርሱ በፈቀደ በመስቀል ላይ በብረቶች ቸነከሩት፤ እርሱም በወደደ ሞትን በሥጋ ቀመሰ፤ እርሱ በፈቀደ ሆምጣጤ ከሐሞት ጋር ቀላቅለው አጠጡት፤ እርሱም በወደደ ነፍሱን ለአባቱ አደራ ሰጠ በማለት ይገልጽልናል፡፡

፪.፲፩ ፍላቭያኖስ

የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ የነበረና የመለኮትና የሰውነት ገጽ ሁለት ነው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም መለኮትና ትስብእት ካልተዋሐዱ ኢሳይያስ አማኑኤል ያለው ማንን ነው? ‹ሥጋዬን ካልበላችሁ ደሜንም ካልጠጣችሁ የዘለዓለም ሕይወት የላችሁም› ያለን ማን ነው? በጲላጦስ ፊት የቆመው፣ የተቸነከረውና የተሰቀለው፣ ዓለምን ያዳነው ማን ነው? በማለት ጥያቄውን በጥያቄ ይመልስለታል፡፡

፫. ነገረ መንፈስ ቅዱስ

፫.፩ መቅዶንዮስ

መንፈስ ቅዱስሕጹጽ› (ፍጡር) ነው” ያለ መናፍቅ ሲሆን በሁለተኛው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ የተወገዘ ነው፡፡ ሊቁ መንፈስ ቅዱስ ከአብና ከወልድ ያነሰ ቢሆን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ሲያዝዛቸውስታጠምቁ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁአለ፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያነሰ ከሆነ ስለምን በማይስተካከለው መጠመቅን አዘዘ? በማለት በጥያቄ ይመልስለታል፡፡

፫.፪ “የመንፈስ ቅዱስ ህላዌ ከክርስቶስ ጥምቀት ወዲህ ነው” ለሚሉ መናፍቃን

እነዚህ መናፍቃን ጌታችን አምላካችን መድኀኒታች ኢየሱስ ክርስቶስ በተጠመቀበት ጊዜ የመንፈስ ቅዱስን በርግብ አምሳል መገለጥ የህላዌው መጀመሪያ አድርገው መናገራቸው እንዴት ስሕተትና ኑፋቄ እንደሆነ የእግዚአብሔር መንፈስ በውኆች ላይ ሰፍፎ ነበር የሚለውን ቃል በመጥቀስና በማብራራት መልስ ይሰጣቸዋል፡፡ ሊቁ እኛ ግንመንፈስ ቅዱስ ቅድመ ዓለም የነበረ ለዘለዓለም የሚኖር ነው› እንላለን በማለት አማናዊውን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ይነግራቸዋል፡፡

ይቆየን

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – ሁለተኛ ክፍል

የካቲት ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፩.፪ አቡሊናርዮስ

አቡሊናርዮስ የሎዶቅያ ሊቀ ጳጳስ ነበረ፡፡ አባ ጊዮርጊስ አቡርዮስ” በማለት ይጠራዋል፡፡ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ለየራስ ናቸው በማለት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ሊቁ ለዚህ መናፍቅ ሲመልስ በአመክንዮ ይጀምራል አስቀድመህ በራስ ፍረድ፤ የሥላሴ ሥርዓት (ሥርዓተ ሥላሴ) ሦስት ከሆነ ማን ፈጠረህ? ማንስ አበጀህ? አብ ራሴን ፈጠረው፤ ወልድም እጄን አበጀው፤ መንፈስ ቅዱስም እግሬን አጸናው ትላለህን? በማለት ይወቅሰዋል፡፡ እንዲህ ካልህ የሥላሴን አንድነት እንደበተንህ የራስህንም አንድነት በተንህ፤የሥላሴን አንድነት እንደ አሕዛብ አማልክት ከፈልኸው፤ ጣዖት ከሚያመልኩ ጋር በሥርዓት ተባበርክ በማለት ይዘልፈዋል፡፡ እኛ ግንአብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ አምላክ፣ አንድ ባሕርይ፣ አንድ መንግሥት፣ አንድ ፈቃድእንላለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ቀጥተኛ አስተምህሮ ይነግረዋል፡፡

የአቡሊናርዮስ ክሕደት የመለኮትንና የሥጋን ተዋሕዶ ሁለት ጊዜ እንደተፈጸመ ያደርገዋል፡፡ ይኸውም በፅንሰት ጊዜ በማኅፀን እና በሞት ተለያይተው የነበሩ ሥጋና መለኮት ከመቃብር በተነሣበት ጊዜ ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም የአቡሊናርዮስ ክሕደት የነፍስ ድኅነትን ያልተፈጸመ የሚያስመስል ነው፡፡ ምክንያቱም ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ነፍስን ካልነሣ ያልነሣውን አላደነምና ነፍስ አልዳነችም ያሰኛል፡፡ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ነፍስን አልነሣም፣ ስለ ልብና ነፍስ ፋንታ መለኮቱ ሆነው ብሎ ያስተማረም ራሱ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስም አንተ አቡሊናርዮስ ሆይ! ቀድሞ በጥርጥርህ አብና ወልድ መንፈስ ቅዱስም የተለያዩ ናቸው ብለህ ከአባቱ የተለየ ነው አልኸው፤ አሁን ደግሞ የክርስቶስ ሰውነት ነፍስና ልብ የለውም፣ መለኮቱም ስለ ነፍስና ልብ ሆነው አልህ፡፡ እንዴት እኮ እርሱ ራሱነፍሴን ፈጽሜ በፈቃዴ እሰጣለሁ› ያለ እንደዚህ ነፍስ የለውም ይባላል?ነፍስ ከሌለው መሞቱ እንደምን ይሆናል? ያለ ነፍስ ከሥጋ በመለየት ሞት የለምና በማለት አፉን ያስይዘዋል፡፡

፩.፫ ቢቱ

ከአባ ጊዮርጊስ ጋር በአንድ ዘመን የነበረ መናፍቅ ሲሆን ለኃጥአን ፍዳ፣ ለጻድቃን በጎ ዋጋ ለመክፈል ወልድ ከአባቱ ተለይቶ ይመጣልየሚል ኑፋቄ ያስተማረ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ቢቱን ሥጋን የለበሰ ሰይጣን፣ ሰው የሆነ ጋኔን ይለዋል፡፡ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ይቀመጣሉ፤ ይመረምራሉ፤ ይፈርዳሉ እንዳለ፣ አባ ጊዮርጊስም ከብሉይና ከሐዲስ ማስረጃዎችን እየጠቀሰ ቢቱን መልስ አሳጥቶታል፡፡ እኛ ግንአብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በሙታንና በሕያዋን ይፈርዱ ዘንድ በአንድ ዐደባባይ፣ በአንዲትም መወቃቀሻ ቦታ ይመጣሉ› እንላለን በማለት ይመልስለታል፡፡

፩.፬ አርዮስ

አርዮስ ወልድ ፍጡር በባሕርየ መለኮቱ፣ ሀሎ ዘመን አመ ኢሀሎ ወልድ፤ ወልድ በባሕርዩ ፍጡር ነው (ሎቱ ስብሐት) … ያልነበረበት ጊዜ ነበር ብሎ ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንም አርዮስን ርእሰ መናፍቃን (የመናፍቃን አለቃ)” ትለዋለች፡፡ አባ ጊዮርጊስ አብ እና ወልድ በባሕርይ፣ በህልውና አንድ እንደሆኑ ከመጻሕፍት ከየወገኑ እየጠቀሰ አፉን ያስይዘዋል፡፡ የክሕደት ቡቃያ አርዮስ ሆይ!እኔና አብ አንድ ነን› ብሎ የተናገረውን የፍጥረታትን ፈጣሪ ፍጡር ትለዋለህን? ዳግመኛምእኔን ያየ አብን አይቷል፤ እኔን የሰማ የላከኝን ሰማው፤ እኔን የካደ የላከኝን ካደው፤ በእኔ ካልሆነ በቀር ወደ አብ መምጣት የሚቻለው የለም፤ የእኔ የሆነው ሁሉ የአንተ ነው፤ የአንተ የሆነው ሁሉ የእኔ ነው›፤ በማለት የተናገረው ፍጡር ነውን? በማለት ፍጹም ሰው ሆኖ የተገለጠው ፍጹም አምላክ እንደሆነ ይመልስለታል፡፡

ስለ ህልውናቸውም የዐይን ጥቅሻ፣ የሽፋሽፍትንም መገለጥ ያህል እንኳ ቢሆን አብ ከወልድ በህልውና መቅደም የለውም በማለት የመለሰለት ሲሆን እኛ ግን ያልተሠራ፣ ያልተፈጠረ፣ ያልጎደለ፣ ያልተለየ እንደሆነ እንናገራለን ይላል፡፡ ፈጽሞ ያልተፈጠረ፣ ያልተሠራ፣ ከአባቱ አኗኗር ያልጎደለና ያልተለየ እንደሆነ እንናገራለን በማለት የወልድን አምላክነት ይመሰክራል፡፡ የአባ ጊዮርጊስ መልስ ዛሬም ኢየሱስ ክርስቶስን ፍጡር ነው” ለማለት “አማላጅ” በሚል ቅጽል ለሚጠሩት ሁሉ መልስ መሆኑን አንብቦ መረዳት የሊቃውንቱንም መልስ የመስጠት መንፈሳዊ ፈሊጥ መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

፩.፭ አርጌንስ

አርጌንስ (ኦሪገን) መዓርገ ርቀትን (‹ቀ› ይጠብቃል) ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አብ ከወልድ እና ከመንፈስ ቅዱስ፣ ወልድም እንደዚሁ ከመንፈስ ቅዱስ እንደሚበልጥ አድርጎ ይናገራል፡፡ ዛሬም በዚህ ኑፋቄ የወደቁና አብ ይበልጠኛል፣ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ አርጋለሁ ብሏል በማለት ኢየሱስ ክርስቶስን ከአብ እንደሚያንስ አድርገው የሚናገሩ አሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ እነዚህን ኀይለ ቃላት እንዲህ ይተረጉማቸዋል፡፡ ከዕርገቱ በፊትወደ አባቴና ወደ አባታችሁ፣ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁያለው ለሰውነት የሚገባ ትሕትናን እያሳየ ነው፤ ለእነርሱ በጸጋ አባታቸው ነው፣ ለእርሱ ግን በእውነት የባሕርይ አባቱ ነው፡፡ ለእነርሱ በእውነት አምላካቸው ነው፤ ለእርሱ ግን ሰው ስለመሆኑ ነው፡፡ ለአርጌንስም እኛ ግን ‹በሥላሴ መዓርግ የመብለጥም ሆነ የማነስ ነገር የለም፤ በመለኮት አንድ ናቸው እንጂ› ብለን እናምናለን በማለት ይመልስለታል፡፡ አርጌንስ ከዚህም በተጨማሪ እግዚአብሔር እንዳይበሉ ከከለከላቸው ዛፍ በበሉ ቀን አዳምንና ሔዋንን ያለበሳቸው ለምድ በእኛ ላይ ያለው የቆዳ ልብስ ነው፤ የቁርበት ለምድ ልብስ አይደለም ማለቱን በመንቀፍ እኛ ግን ሥጋስ ቀድሞም በተፈጠሩ ጊዜ አላቸው፤ በኋላ እግዚአብሔር ያለበሳቸው ግን የቁርበት ልብስ ነው፤ ትእዛዙን ስላቃለሉ የነቀፋ ልብስ ነው እንላለን ብሎ ይመልስለታል፡፡

፪. ምሥጢረ ሥጋዌ (ነገረ ክርስቶስ)

፪.፩ ንስጥሮስ

ንስጥሮስ የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ የነበረ ሲሆን የክርስቶስን አካልና ባሕርይ ለሁለት በመክፈል ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ በማለት ኅድረትን ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ወልድንከነቢያት አንዱ ነው፤ የዮሴፍ ልጅ ነው› ለማለት እንዴት ደፈርህ?” የሚለው ስለዚህ ነው፡፡ ንስጥሮስ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የሰው እናት (Anthropothokos) እንጂ የአምላክ እናት (Theotokos) መባል የለባትም ያለ መናፍቅ ነው፡፡ በእርግጥ ያሻሻለ መስሎ የክርስቶስ እናት (Christotokos) እላታለሁ” ብሏል፡፡ ይህን ቢልም ግን ለንስጥሮስ ክርስቶስ እግዚአብሔር ያደረበት ደግ ሰው እንጂ አምላክ አይደለም (ሎቱ ስብሐት)፡፡ ለዚህ ነው አባ ጊዮርጊስ ንስጥሮስን እመቤታችን ማርያምን መለኮት ያደረበትን ሰው የወለደች እንጂ የአምላክ እናት እንደማይሏት ስለ ልጆችህ ዜና ሰማን በማለት የሚዘልፈው፡፡

ሊቁ ለዚህ ኑፋቄው መልስ ሲሰጥ በእውነት ኢየሱስ ክርስቶስ ዐመጽ የሌለበት አምላክ፤ ኃጢአት የሌለበት ሰው፤ እድፍ የሌለበት ንጹሕ በግ፤ ነውር የሌለበት ፍሪዳ፤ ርኵሰት የሌለበት የበሰለ ኅብስት፤ አተላ የሌለው የጠራ የወይን ጭማቂ፤ የተወደደ ዕጣን፤ የሚያንጸባርቅ ሽቱ፤ የሕዝብን ኃጢአት ይቅር የሚል ኃጢአት የሌለበት ካህን፤ ፊት አይቶ ለሀብታም፣ ለደሀ የማያዳላ ንጉሥ ነው በማለት አምላክ ወሰብእ መሆኑን ይመሰክራል፡፡ ስለ እመቤታችንም ቀድሞ እግዚአብሔር ወልድ ከእግዚአብሔር አብ እንደተወለደ፣ በኋለኛው ዘመን የእግዚአብሔር አንድያ ልጅ ከብቻዋ ከድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ በመጀመሪያ የማይታይ እርሱ ከማይታየው ተወለደ፤ በኋላም የማይያዝ የሕይወት እሳት፣ ከምትዳሰስ ሥጋ ተወለደ፡፡ በመጀመሪያ የሀልዎቱ መጀመሪያ ሳይታወቅ ተወለደ፤ በኋላም የዘመናት ፈጣሪ ዓመታትንም የሚወስን እርሱ ዕድሜዋ ዐሥራ አምስት ዓመት ከሆነ ከታናሽ ብላቴና ተወለደ፡፡ የመጀመሪያ ልደቱን ምሥጢር የኋለኛ ልደቱንም ድንቅ አደረገ በማለት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ መሆኗን በማስረዳት ከብሉያትና ከሐዲሳት እየጠቀሰ ያሳፍረዋል፡፡ ከሥጋዌ በኋላ ምንታዌ እንደሌለም የአርዮስን ክሕደት በዘለፈበት ድርሳኑ ሰው ከሆነ በኋላ በመለኮቱ የእግዚአብሔር ልጅ፣ በሰውነቱ የማርያም ልጅ አንለውምበማለት ይነግረናል፡፡

፪.፪ የሮሜ ሊቀ ጳጳስ ልዮን

ርጕም ልዮን በሦስተኛው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ (ጉባኤ ኤፌሶን) ሁለት መቶ ሊቃነ ጳጳሳት ተሰብስበው ያወገዙትን የንስጥሮስን ክሕደት በማሻሻል አንድ አካል ሁለት ባሕርይ” የሚል ክሕደት የጀመረ መናፍቅ ነው፡፡ ለቤተ ክርስቲያን መከፈልም ተጠያቂ ነው፡፡ ልዮን ሥጋ ከመለኮት ያንሳል ይላል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ” የተባለ አባ ጊዮርጊስ እኔ እና አብ አንድ ነን፤ ከሰማይ የወረደ ኅብስት እኔ ነኝ፤ ባለመድኃኒት ከሰማይ መጣ …” የሚሉትን ንባባት በመተርጎም እኛ ግን ‹ከተዋሕዶ በኋላ የክርስቶስ ትስብእት ከመለኮቱ አያንስም (አይጎድልም)› እንላለን፡፡ ባለመድኃኒት በድውዮች ሴት ልጅ ዘንድ አደረ፤ ከእርሷም ምድራዊት ሥጋን ተዋሐደ፡፡ ለድውዮችም ፈውስ በሚሆን ገንዘብ ከመለኮቱ ጋር አንድ አደረገው፡፡ ባለመድኃኒት ከሰማየ ሰማያት መጥቷልና የፈውስ እንጨት በዳዊት ቤት ተገኘ፡፡ ያለመለኮት ከሥጋ ጋር መዋሐድ ፈውስ እንደማይገኝ ባለመድኃኒቱ ዐወቀ፤ ስለዚህም ራሱን ሰው ለመሆን ሰጠ፡፡ ታማሚስ ለራሱ ፈውስን ያደርግ ዘንድ አይቻለውም፤ ነገር ግን በሚድንበት ገንዘብ መድኃኒት እንዲያደርግለት ባለመድኃኒቱን ይማልደዋል በማለት አፉን ያስይዘዋል፡፡

፪.፫ የኬልቄዶን ማኅበርተኞች

በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ጉባኤ ከለባት በመባል በሚጠራው በኬልቄዶን ጉባኤ የተሳተፉት ስድስት መቶ ሠላሳ ስድስት ኤጲስቆጶሳት ናቸው፡፡ እነዚህ ጉባኤተኞች መለኮትና ሥጋን በመለያየት ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ ናቸው” የሚል እንግዳ ትምህርት ያመጡ ናቸው፡፡ አባ ጊዮርጊስም መለኮት በሰውነት ሥጋ እንደሆነ፤ ሰውነትም በመለኮት አምላክ ሆነ፡፡ በመለኮቱ መቀየርን ስለ ሰውነቱም መለወጥን አናስብ፤ ስለ አንድነቱ መቀላቀልን፣ ስለ ባሕርይውም መለያየትን አናስብ፡፡ እርሱ በመለያየት ያልተከፈለ፣ በወንድማማችነትም ሁለት ያልሆነ ነው፡፡ በመለኮቱም በሰውነቱም አንድ እግዚአብሔር ነው በማለት መልስ ሰጥቷቸዋል፡፡ እኛ ግንከድንግል ማርያም ሰው የሆነ አንድ አካል አንድ ባሕርይ (ፈቃድ) ነውእንላለንበማለትም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ አስረድቷቸዋል፡፡

ይቆየን

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – የመጀመሪያ ክፍል

የካቲት ፳፯ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ዕቅበተ እምነት የቤተ ክርስቲያን የዕለት ከዕለት አገልግሎት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ በጎላና በተረዳ ለመናገር የዐቃብያነ እምነት ዘመን የሚባል ወቅት ቢኖርም ቤተ ክርስቲያን የዕቅበተ እምነት ተግባር ያልፈጸመችበት ጊዜ የለም፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በቃልም በመጽሐፍም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ያስጠበቁ ብዙ ሊቃውንትን እናገኛለን፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ከእነዚህ ስመ ጥር ዐቃብያነ እምነት ውስጥ አንዱ ነው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በድርሰቱ ዳግማዊ ያሬድ”፣ በመንፈሳዊ ዕውቀቱ ዐምደ ሃይማኖት”፣ መናፍቃንን ተከራክሮ በመርታቱ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ” ተብሎ ይጠራል፡፡

ዜና ገድሉን የጻፈው ሊቁ ወልደ አብ እንደ ሙሴ የኦሪት መምህር፣ እንደ ሄኖክ የተሰወረውን የሚያይ፣ እንደ ኤልያስ ለአምላኩ ሕግ የሚቀና፣ እንደ ኢሳይያስ ልዑለ ቃል (ቃሉ ከፍ ያለ)፣ ጎልያድን የገደለው ዐዲሱ ዳዊት፣ የመንግሥተ ሰማያት መክፈቻዎችን የተቀበለ ጴጥሮስ፣ ከኢየሩሳሌም እስከ እልዋሪቆን ያስተማረ ልሳነ ዕፍረት ጳውሎስ፣ …” (ገድለ አባ ጊዮርስ ምዕራፍ ፩፡፲፮-፲፰) በማለት ክብሩን ልዕልናውን ይገልጸዋል፡፡ የሊቁን ዜና ዕረፍት በሰሙ ጊዜ ንጉሡና ሕዝበ ክርስቲያኑ ያለቀሱት ለቅሶ የአባ ጊዮርጊስን ጸጋና ተወዳጅነት የሚያስረዳ ነበር፡፡ አባ ቸር ጠባቂ፣ አባ የምስጋና ክቡር ዕቃ፣ አባ ዐዲሱ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ አባ ቀዩና አረንጓዴው ወርቅ፣ አባ ሰማያዊ ሰውና ምድራዊ መልአክ፣ አባ የማይዛባ የሃይማኖት ምሰሶ፣ አባ የኢትዮጵያ ብሩህ ፀሐይና በምልዐቱ የሚታይ ጨረቃ፣ አባ ሰማያዊ ኮከብ፣ በእውነት መለኮታዊ እሳት የተዋሐደውን ቅዱስ ቍርባን የዳሰሱ እጆችህ ደረቁን? እግሮችህስ በሞት መግነዝ ተገነዙን? አባ በእውነት ዐይኖችህ ተከደኑን? አፍንጮችህስ ተዘጉን? አፍና ከንፈሮችህስ ተከደኑን? …” በማለት ነበር ኀዘናቸውን የገለጹት፡፡

አባ ጊዮርጊስ በመጻሕፍት አዋቂነቱ እና በቅድስናው የተመሰከረለት አባት ነው፡፡ በተለያዩ ጊዜያት የተነሡ የመናፍቃንን ጥያቄዎች በቃልም በመጽሐፍም በመመለስ ይታወቃል፡፡ በገድሉ ላይ ተጠቅሰው ከምናገኛቸው የቃል ክርክሮች አንዱ የአይሁዳዊው ታሪክ ነው፡፡ በአንድ ወቅት አንድ አይሁዳዊ ጌታችሁ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆነአልዓዛርን የት ቀብራችሁት?› ብሎ ለምን ጠየቀ?” ብሎ በጠየቀ ጊዜ አባ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አብ በኦሪት ለምንአዳም ሆይ ወዴት ነህ?› ብሎ ጠየቀው? አብርሃምንስሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?› ብሎ ለምን ጠየቀው?” በማለት እንዳሳፈረው በገድሉ ተጽፏል፡፡

አባ ጊዮርጊስ ብዙ ድርሳናትን ደርሷል፤ የሚበዙት የምስጋና ድርሰቶች ናቸው፡፡ ከጻፋቸው ብዙ መጻሕፍት መካከል አንዱ መጽሐፈ ምሥጢር ነው፡፡ መጽሐፈ ምሥጢር በቤተ ክርስቲያናችን ከሚጠቀሱ የዕቅበተ እምነት መጻሕፍት ውስጥ አንዱ ሲሆን የአባ ጊዮርጊስ የነገረ ሃይማኖት ሊቅነቱ የተመሰከረበት መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፉ አባ ጊዮርጊስ በነገረ እግዚአብሔር ላይ ጽርፈት የተናገሩ መናፍቃንን ለመገሠጽና ለእነርሱ መልስ ለመስጠት የጻፈው መጽሐፍ ነው፡፡ በምን ዓይነት ቅንዐተ መንፈስ ቅዱስ ተነሣሥቶ መልስ እንደሰጠ ሲነግረን “… የቅዱሳንን ዜናቸውን ለመናገር ፍቅር ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ከሐዲዎችን እነቅፋቸው ዘንድ ያስገድደኛል፤ ፍቅር ክርስቶስን እንዳመሰግነው ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ሰይጣንን አወግዘው ዘንድ ያስገድደኛል፤ ፍቅር የክርስቶስን ሐዋርያት እንድከተላቸው ያስገድደኛል፤ ቅንዐትም ዝንጉዎችን እንድዘልፋቸው ግድ ይለያኛል፤ ፍቅር ሰማዕታትን አወድሳቸው ዘንድ ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ጠንቋዮችን እንድዘልፋቸው ያስገድደኛልበማለት ይገልጽልናል፡፡

አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በዚህ መንፈሳዊ ቅናቱ ምክንያት እግዚአብሔር የገለጠለትን ምሥጢር አምስት ጸሐፊዎችን ሰብስቦ እርሱ በቃል እየነገራቸው በሁለት ዕለታት ጽፈውታል፡፡ መጽሐፉ ሲያልቅ ጸሓፊዎቹ እጅግ አደነቁ፡፡ ምሥጢረ እግዚአብሔርን እየሰማ ያጻፈው አባ ጊዮርጊስም ጽሑፉን ተመልክቶ አደነቀ፤ እኔ የዚህን መጽሐፍ ቃል አልተናገርኩም፤ መንፈስ ቅዱስ በእኔ አንደበት ተናገረ እንጂ በማለት ተናግሯል፡፡ ይህንም መጽሐፍ የመለኮትን ነገር ይናገራልና መጽሐፈ ምሥጢር”  ሲል ሰየመው፡፡ መጽሐፉ በመጀመሪያ የተጻፈው በግእዝ ቋንቋ ሲሆን አሁን ግን ወደ አማርኛ ተተርጕሞ በብዙዎች እጅ ደርሷል፡፡

የመጽሐፈ ምሥጢር አጻጻፍ ወይም መልስ አሰጣጥ ስልትን ስንመለከት አባ ጊዮርጊስ በየምዕራፉ በምስጋና ይጀምራል፡፡ ከምስጋና ቀጥሎ መልስ የሚሰጣቸውን መናፍቃን ኑፋቄና ጥንተ ታሪክ ይገልጻል፡፡ ደርሰውበት የነበረውን የክህነት መዐርግ ጠቅሶ ከተናገሩት የክሕደት አዘቅት ጋር በማወዳደር ይወቅሳቸዋል፡፡ ከዚያም ለኑፋቄያቸው የተራቀቀ የነገረ ሃይማኖት ዕውቀቱን ተጠቅሞ ከብሉይና ከሐዲስ እየጠቀሰ መልስ ይሰጣል፡፡ በመልሱ ውስጥ በብሉይም ሆነ በሐዲስ የተነገሩ ትንቢትና ምሳሌዎችንም መንፈስ ቅዱስ በገለጠለት መሠረት ትርጉም ለአንባብያን ግልጥ እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ አባ ጊዮርጊስ ለመናፍቃኑ መልስ በአብዛኛው የጠቀሰው ከብሉይና ከሐዲስ ነው፡፡ ከቅዱሳት መጻሕፍት እየጠቀሰ ለመናፍቃኑ መልስ የሰጠበትን ክፍል ዘለፋ፣ ወቀሳ” ይለዋል፡፡

ሊቁ በእግዚአብሔር ላይ የነቀፋ ቃል የተናገሩትን ይዘልፋቸዋል፣ ይገዝታቸዋል፣ ይረግማቸዋል፡፡ በሥላሴ ላይ የነቀፋ ቃል ባይናገሩም እንኳን የተሳሳተ ትምህርት ያስተማሩትን ደግሞ በጽድቅ ጎዳና ስላልቆሙ እንዘልፋቸዋለን፤ ርግማን ግን በሥላሴ ላይ ሐሰት ስላልተናገሩ አንረግማቸውም በማለት በተግሣጽ ያልፋቸዋል፡፡ በየአርእስቱ መጨረሻም በሃይማኖት አባቶቹን እንደሚመስል በምግባር ግን ደካማ እደሆነ በመጥቀስ አንባብያን በጸሎት እንዲያግዙት በመማጸን ያጠቃልላል፡፡ ይህም ቅዱስ ጴጥሮስ በእናንተ ስላለ ተስፋ ምክንያትን ለሚጠይቋችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት ዘወትር የተዘጋጃችሁ ሁኑ፤ ነገር ግን በየዋሕነትና በፍርሃት ይሁን (፩ኛ ጴጥ. ፫፡፲፭) ያለውን ፍርሃትና የዋህነት የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጸሎትና በልመናም ሁሉ ዘወትር በመንፈስ ጸልዩ በዚህም አሳብ ስለ ቅዱሳን ሁሉ እየለመናችሁ በመጽናት ሁሉ ትጉ፤ ዳግም የወንጌልን ምሥጢር በግልጥ እንዳስታውቅ አፌን በመክፈት ቃል ይሰጠኝ ዘንድ፣ ስለ እኔ ለምኑ፤ ስለ ወንጌልም በሰንሰለት መልእክተኛ የሆነው መናገር እንደሚገባኝ ስለ እርሱ በግልጥ እናገር ዘንድ ለምኑ በማለት እንዳስተማረው፡፡

አባ ጊዮርጊስ በመጽሐፉ ለአሕዛብ፣ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ለሚታወቁ መናፍቃንና በዘመኑ ለተነሡ እንደ ቢቱ ላሉ መናፍቃን መልስ ሰጥቷል፡፡ አጠቃላይ መልስ የሰጠባቸውን ርእሰ ጉዳዮች ስናይ ምሥጢረ ሥላሴ፣ ምሥጢረ ሥጋዌ፣ ነገረ ክስቶስ፣ ነገረ መንፈስ ቅዱስ፣ ነገረ ማርያም ላይ ያተኮሩ ሲሆኑ በአንድ ማሕቀፍ ሥር የማይጠቃለሉ ለሌሎች ልዩ ልዩ ጉዳዮችም መልስ ሰጥቷል፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዋና ዓላማ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተለያዩ ዘመናት የተነሡ መናፍቃንና ከሐዲያን  ላነሧቸው የኑፋቄ ትምህርቶች የሰጠዉን መልስ በማሳየት ምእመናን ከመሰል ክሕደቶች እንዲጠበቁ ማድረግ ነው፡፡ የእኛ ታሪክ አለማወቅ እንጂ አዲስ ኑፋቄም፤ አዲስ ትምህርትም አለመኖሩን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ለሚያጠና በሦስቱ ዓለም አቀፍ ጉባኤያት መልስ የተሰጠባቸውን ኑፋቄዎች አባ ጊዮርጊስ የጻፈውን መጽሐፈ ምሥጢር በቅርቡም መልአከ ብርሃን አድማሱ ጀንበሬ እና አለቃ አያሌው ተአምሩ የሰጧቸውን መልሶች ማየት ተገቢ ነው፡፡

ከሐዋርያት ጀምሮ እስከ ዘመነ ሊቃውንት ለተነሡት መናፍቃን የቤተ ክርስቲያን አባቶች መልስ ሰጥተዋል፡፡ ጉባኤ ዘርግተው፣ ተከራክረው መንፍቃንን አሳፍረው መልሰዋል፡፡ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ የቀደሙ አባቶችን አክሎና መስሎ ቅዱሳት መጻሕፍትን በመተርጎምና የሊቃውቱን ቃል በማራቀቅ መልስ በመስጠቱ የአባቶቹ የግብር ልጅ መሆኑን አስመሰከረ፤ የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሯችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፣ የኑሯቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሏቸው የሚለውንም አሳየን፡፡ ስለ ምሥጢረ ሥላሴ ከሰጠው ትምህርት መካከልም የሚከተለው ኃይለ ቃል ተጠቃሽ ነው፤ አብ ብርሃን አንደሆነ ወልድም ለሰው ሁሉ የሚያበራ ብርሃን ነው፡፡ ወልድ ብርሃን እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም ፍጹም በሆነ አንድ ጸዳል ያለ ብርሃን ነው፡፡ አብ የማይዳሰስ እሳት እንደሆነ ወልድም የማይያዝ እሳት ነው፡፡ ወልድ የማይያዝ  እሳት እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም በሃይማኖት ሙቀት ቤተ ክርስቲያንን የሚያሞቃት እሳት ነው፡፡ አብ የማይታይ ኃይል እንደሆነ ወልድም ሰው በመሆኑ ካልሆነ በቀር የማይገለጥ ኃይል እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም ከጥፋት ሰዎች መነሣሣት የተነሣ እንዳትናወጽ ቤተ ክርስቲያንን የሚጠብቃት ኃይል ነው፡፡ አብ ፍጹም አምላክ እንደሆነ ወልድም ፍጹም አምላክ ነው፡፡ ወልድ ፍጹም አምላክ እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም በአንድ ኅብር መልክእ ያለ ፍጹም አምላክ ነው፡፡

ከዚህ በመቀጠል መናፍቃን አንሥተዋቸው ሊቁ በመጽሐፈ ምሥጢር ኦርቶዶክሳዊ መልስ የሰጠባቸውን ዋና ዋና ጉዳዮች እናቀርባለን፡፡

፩. ምሥጢረ ሥላሴ

፩.፩ ሰባልዮስ

ሰባልዮስ በአባ ጊዮርጊስ አጠራር ሰብልያኖስ” ተብሎ ተጠቅሷል፡፡ በሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሣ መናፍቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር አንድ ገጽ ነው፤ አንዱ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን አብ፣ በሐዲስ ኪዳን ወልድ፣ በበዓለ ኀምሳ ደግሞ መንፈስ ቅዱስ ሆኖ ተገለጠይላል፡፡ በአጭሩአብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ አንድ ገጽ ነው የሚል የኑፋቄ ትምህርት ያስተማረ መናፍቅ ነው፡፡ በሊቃውንቱ ቋንቋ የሰባልዮስ ኑፋቄ አንድ ገጽ (ሞናርኪያኒዝም) ሲባል ተከታዮች ደግሞ ሰባልዮሳውያን” ይባላሉ፡፡ የሥላሴን አካላት አንድ አድርገው በመናገራቸውም ሰቃልያነ አብ ይባላሉ፡፡ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ለሰባልዮስ ከብሉይ ከሐዲስ እየጠቀሰ መልስ ሰጥቷል፡፡ ሊቁ እኛ ግን ሦስት ገጽ አንድ ባሕርይ፣ ሦስት አካል አንድ አምላክ፣ ሦስት ስሞች አንድ እግዚአብሔር እንላለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ይመሰክራል፡፡ ሰባልዮስንም ተጠራጣሪ ሆይ እንግዲህ ባንተ ያለውን ክሕደት ትተህ በሥላሴ እመን፤ ለሥላሴ ገጻትም ምስጋናን አቅርብ በማለት ይመክረዋል፡፡

ይቆየን

መጽሐፍ ቅዱስ በቤተ ክርስቲያን ዐይን

የካቲት ፳፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ የታነፀች፣ ከሁሉ በላይ የሆነች አንዲትና ቅድስት አካለ ክርስቶስ ናት (ኤፌ. ፩፥፳፪፤ ኤፌ. ፪፥፳)፡፡ ‹‹ከሁሉ በላይ የሆነች›› የሚለው ሐረግ ሰማያዊ ሥልጣኗን እና ልዕልናዋን የሚገልጽ ነው፡፡ ይህም ማለት የትኛውም ቅዱስ መጽሐፍ ወይም ንዋይ በእርሷ ውስጥ ይሆናል እንጂ ከበላይዋ ሊሆን አይችልም ማለት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን የገለጸውን እውነት የያዘ እንጂ ከቤተ ክርስቲያን በላይ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካል ስለሆነች ከክርስቶስ አካልነት በላይ የሆነ ስለሌለ ነው፡፡ ከቤተ ክርስቲያን በላይ ያለ የቤተ ክርስቲያን ራስ ክርስቶስ ብቻ ነው (ቆላ. ፩፥፲፰)፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የመጻሕፍት ሁሉ ራስ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን ደግሞ የመጽሐፍ ቅዱስ ባለቤት ናት፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ በሰዎች ቋንቋ የተጻፈ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ የተጻፈውም በመንፈስ ቅዱስ ምሪት ነው፡፡ ጸሓፊዎቹ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ናቸው፡፡ በቅድስናቸው ለእግዚአብሔር ቅሩባን ስለሆኑ የእግዚአብሔር ቃል ለሚላክላቸው አብያተ ክርስቲያናት በሚገባቸው ቋንቋ ጽፈዋል፡፡ መጻፋቸውም የእነርሱን ክብር ለመግለጽና ቤተ ክርስቲያን የምትመራበትን ሕግ ለመደንገግ ሳይሆን ቤተ ክረስቲያን የምታምነውን እምነት ለመመስከርና በመንፈሳዊ ሕይወት ውጣ ውረድ ውስጥ ያሉ ምእመናን እንዲመከሩበት፣ እንዲገሠጹበት፣ ልባቸውን እንዲያቀኑበት ነው፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን የገለጠውን እውነትና ቤተ ክርስቲያን ስለ እግዚአብሔር የምታምነውን እምነት የያዘ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ተሰፍሮና ተቈጠይሮ ሁሉ ነገር የተካተተበት ማለት አለመሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

ቤተ ክርስቲያን በማየት፣ በማድረግ፣ በቃል የሚተላለፍ ብዙ ሀብት አላት፡፡ እንዲያውም የተጻፈው በጣም ጥቂቱ ነው፡፡ ሆኖም በአንዳንድ የእምነት ድርጅቶች ዘንድ ነገረ ቤተ ክርስቲያንን በሙሉ ጠቅልሎ በመጽሐፍ ሥር የማድረግ የተሳሳተ አካሔድ አለ፡፡ ይህም በሉተራውያን ዘንድ “Sola Scriptura” ወይም “Only Bible” (መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ) ተብሎ የሚታወቀው ሲሆን ያልተጻፈው ቅዱስ ትውፊትም ሆነ መጽሐፍ ቅዱስ የማይደግፈው ግለሰባዊ አሳብ እንጂ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት አይደለም፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት መጻሕፍትን የምትቀበልበትን ሃይማኖታዊ እይታ በግልጽ ማሳየት ነው፡፡

የቅዱሳት መጻሕፍት ጥንተ ታሪክ

ፈጣሬ ኵሉ ዓለም እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ፍጥረታት ሁሉ እጅግ አክብሮ የፈጠረው የሰው ልጅን ነው፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይህን ክብሩን ሲገልጹ ሰውን “የፍጥረታት አክሊል – The Crown of Creation” ብለው ይጠሩታል፡፡ የፍጥረታት አክሊልነቱም በእግዚአብሔር አርአያና ምሳሌ መፈጠሩ፣ ፍጥረታትን ሁሉ ከእግዚአብሔር በታች እንዲገዛ በፍጥረታት ላይ መሠልጠኑ ነው፡፡ እግዚአብሔር “ሥሉጥ በላዕለ ኵሉ ፍጥረት፤ በፍጥረት ሁሉ ላይ የሠለጠነ (ሥልጣን ያለው)” እንደሆነ ሁሉ ሰውንም በጸጋ “ሥሉጥ በላዕለ ኵሉ ምድር፤ በምድር ሁሉ ላይ የሠለጠነ (ሥልጣን ያለው)” አድርጎታል፡፡ በጥንተ ተፈጥሮው የሰው ልጅ መጻሕፍትም ሆኑ መምህራን የማያስፈልጉት ዐዋቂ ፍጥረት ነበር፡፡ እንደ አባ ማቴዎስ በአእምሮ ጠባይዕ፣ እንደ አብርሃምና እንደ ሙሴ ጸሊም በሥነ ፍጥረት ተመራምሮ የሚያውቅ ማለት ነው (ትርጓሜ ወንጌለ ዮሐንስ)፡፡ በለባዊ አእምሮው ሥነ ፍጥረትን አንብቦና መርምሮ ረቂቁን እውነት የሚረዳ ከሃሊ ዘበጸጋ ነበር፡፡ የሰው የመጀመሪያ መጽሐፍም ሥነ ፍጥረት ነው፡፡ ለሰው የመጀመሪያ እውነተኛ መምህሩ መምህረ ኵሉ ዓለም እግዚአብሔር ነው፡፡

እግዚአብሔር ለአዳም ትእዛዛቱን አስተማረው፡፡ ከመጀመሪያ ትምህርቶቹም ዋናው “ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና” (ዘፍ. ፪፥፲፮-፲፯) የሚለው ነበር፡፡ አዳም ግን እውነተኛ መምህሩን ትቶ የክፉ ፍጡር ትምህርትን ተማረ፤ “ሞትን አትሞቱም፤ ከእርስዋ በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንዲከፈቱ እንደ እግዚአብሔርም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንድትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው እንጂ” (ዘፍ. ፫፥፬-፭) ብሎ ሰይጣን የነገረውን ሰማ፡፡ ተማሪው ከሁለቱ ትምህርቶች ሁለተኛውን መረጠና በፈተና ወደቀ፡፡ የመጀመሪያ መምህሩን ትምህርት ይረዳም ዘንድ ከዚያ በኋላ ብቁ ልቡና አልነበረውም፡፡ ወደ ታላቁ መምህር ለመመለስ ሌሎች መምህራን እንዲደግፉት ግድ ሆነ፡፡

ክፉው መምህር ካሳታቸው በኋላ አዳምና ሔዋን ያልተጻፈውን ፊደል አዩ፣ ያልተከተበውን አነበቡ፡፡ “ሴቲቱም ዛፉ ለመብላት ያማረ እንደ ሆነ፥ ለዓይንም እንደሚያስጎመጅ፥ ለጥበብም መልካም እንደ ሆነ አየች (ዘፍ. ፫፥፮) እንዲል፡፡ ከዚህም በኋላ ፍጥረታትን የሚያነቡ ሳይሆኑ ፍጥረታት የሚያስደነግጡአቸው ድንጉጦች ሆኑ፡፡ እግዚአብሔር ካደላቸው ከንጽሐ ጠባይ ደረጃ ስለወደቁና ወደ ቀደመ ክሂሎታቸው መመለስ ስላልቻሉ በሰውኛ ፊደል የተጻፉ መጻሕፍትን በማንበብ መመርኮዝ ግድ ሆነባቸው፡፡ የሰው ልጅ ፍጡር ባልሆነ ብርሃን ረቂቁንና የማይታየውን ዓለም ከማየት እና በማየት ከሚገኘው ዕውቀት ከመስማት ወደሚገኘውና ውስን ወደሆነው ዕውቀት በመውረዱ ምክንያት መጽሐፍ አስፈለገው፡፡ ስለዚህ መጻሕፍት የሰው የባሕርዩ መምህራን አይደሉም፡፡ ከውድቀቱ በኋላ የተሰጡት ደጋፊዎች እንጂ፡፡ ይህንም የቤተ ክርስቲያን መምህራን በሚከተለው ምሳሌ ይገልጹታል፤

ሰው የሚራመደው በሁለት እግሩ ነው፡፡ እግሩን ሲታመም ወይም ሲያረጅ በሁለት እግሩ መራመድ ስለሚያቅተው ምርኩዝ ይይዛል፡፡ ልክ እንደዚሁ ሰው በቅድመ ተፈጥሮው በራሱ መቆምና መራመድ የሚችል ነበር፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ካረጀና ከታመመ በኋላ መቆምም መራመድም ይችል ዘንድ መጻሕፍትና መምህራን ምርኩዝ እንዲሆኑት ተሰጡት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው ይህን ይበልጥ ሲያብራራልን “በቀለም ከተቀረፁ የመጻሕፍት ቃላት ይልቅ በልቡናችን ያደረ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይመራን ዘንድ እጅግ ንጹሕ ሕይወት ሊኖረን እንጂ የተጻፈ ነገር ሊያስፈልገን አይገባም ነበር” ብሏል፡፡ ይህን ካለ በኋላ ግን መጻሕፍትን በጥንቃቄ መያዝ እንደሚገባን ሲያስተምረን “ይህን ጸጋ ከእኛ እንዲርቅ አድርገናል፡፡ እንግዲህ ሁለተኛውን ታላቅ ስጦታ (መጻሕፍትን) አጥብቀን እንያዝ” ብሏል፡፡ ይህ ሁሉ ቅዱሳት መጻሕፍት ከጊዜ በኋላ አስፈላጊ በመሆናቸው የተሰጡ እንጂ ሁሉ ነገር ከእነርሱ የጀመረ አለመሆኑን የሚያስረዳ  ነው፡፡

ወንጌል ከተጻፈውም በላይና የቀደመች እንደሆነች

ብዙ ጊዜ ወንጌል ስንል አራቱ የወንጌላውያን መጻሕፍት ብቻ ቀድመው ይታሰቡን ይሆናል፡፡ አንዳንድ “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” የሚሉ የእምነት ድርጅቶች እንደሚሉትም የተጻፈው ብቻ ወንጌል የሚመስለንም እንኖር ይሆናል፡፡ የተጻፈውም ሆነ ያልተጻፈው ቅዱስ ትውፊት ግን ወንጌል በጽሑፍ ብቻ የተገደበ እንዳልሆነ ያስተምረናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ወንድሞች ሆይ፥ የሰበክሁላችሁን ደግሞም የተቀበላችሁትን በእርሱም ደግሞ የቆማችሁበትን በእርሱም ደግሞ የምትድኑበትን ወንጌል አሳስባችኋለሁ፤” ሲል አራቱ ወንጌላት ተጠቃለው አልተጻፉም ነበር (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፩)፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ወንጌል በዓለም ሁሉ በማናቸውም ስፍራ በሚሰበክበት እርስዋ ያደረገችው ደግሞ ለእርስዋ መታሰቢያ እንዲሆን ይነገራል” ብሎ ስለ ማርያም እንተ ዕፍረት በመሰከረ ጊዜ ማቴዎስም፣ ማርቆስም፣ ሉቃስም፣ ዮሐንስም ገና ወንጌልን አልጻፉም ነበር (ማቴ. ፳፮፥፲፫)፡፡ ይህ ቃል በተነገረ ጊዜ እንኳን ወንጌልን ሊጽፉ እምነታቸውም የተሟላ አልነበረም፡፡ ይህም በመከራው ጊዜ ከዮሐንስ በስተቀር ሁሉም በመሸሻቸው ተገልጧል፡፡ ስለዚህ ጌታ “ይህ ወንጌል” ሲል የተጻፈውን ብቻ የምናስብ ከሆነ ስሕተት መሆኑን ልብ ይሏል፡፡

ወንጌል በቃልም፣ በመጽሐፍም፣ በሕይወትም የምትሰበክና የተሰበከች እንጂ በመጻሕፍት ተጠቃላና ተካትታ የተቀመጠች ብቻ አድርጎ ማሰብ ስሕተት ነው፡፡ ሐዋርያት በቃልም በመጽሐፍም ሰብከዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ በሕይወቱ ባገኘው መገለጥ ተሰብኳል (ሐዋ. ፱)፡፡ እንዲያውም የቅዱሳት መጻሕፍት ጸሐፍያን በጽሑፍ የተሰበከው ጥቂት መሆኑንና በቃል ብዙዎች እንደተሰበኩ ገልጸዋል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌሉን ጽፎ ሲያጠቃልል “ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል” (ዮሐ. ፳፩፥፳፭) የሚለው ሁሉ ነገር አለመጻፉን ያስረዳል፡፡ ስለዚህ ከተጻፉት በላይ ቤተ ክርስቲያን በትውፊት ያቆየችልን ብዙ ነገር መኖሩን መረዳት ተገቢ ነው፡፡

ቅዱስ ሉቃስም ገና ወንጌሉን መጻፍ ሲጀምር ለሚጽፍለት ቴዎፍሎስ ለተባለው ሰው “የከበርህ ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ከመጀመሪያው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን፥ በኛ ዘንድ ስለ ተፈጸመው ነገር ብዙዎች ታሪክን በየተራው ለማዘጋጀት ስለ ሞከሩ፥ እኔ ደግሞ ስለ ተማርከው ቃል እርግጡን እንድታውቅ በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ልጽፍልህ መልካም ሆኖ ታየኝ” (ሉቃ. ፩፥፩-፬) ብሏል፡፡ ይህ በዓይን ያዩ፣ ወንጌልን ሳይጽፉ በቃል ወይም በሌሎች መጻሕፍት ያስተማሩና ለነቅዱስ ሉቃስም ያስተላለፉ መኖራቸውን በቅድሚያ ሲያስረዳ ወንጌሉ የተጻፈለት ቴዎፍሎስ እንኳን አስቀድሞ በቃል መማሩንም የሚያሳይ ነው፡፡ ቅዱስ ሉቃስም እርግጡን ያውቅ ዘንድ ወይም ያረጋግጥ ዘንድ ጻፈለት እንጂ ከዚያ በፊት ያልተማረ ስላልነበር ለማስተማርና ለማሳወቅ የጻፈለት አይደለም፡፡

ከመጽሐፍ ቅዱስና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቱ ይቀድማል?

ቤተ ክርስቲያን ከመጽሐፍ ቅዱስ በፊት የነበረችና መጽሐፍ ቅዱስን የጻፈች፣ ከእግዚአብሔር የተቀበለችውን በመጽሐፍ የተቀመጠውን እውነት ጠብቃ ያስተላለፈች የእግዚአብሔር መንግሥት ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው በቤተ ክርስቲያን ለቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ከተጻፉት መጻሕፍትም ውስጥ አምላካውያት የሆኑትን በቀኖና ለይታና ቀድሳ ለምእመናን የሕይወት ምግብነት የሰጠች መሆኗን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ከመጽሐፍ ቅዱስ ትቀድማለች፤ መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ለመሆኑም ምስክሯ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ምሪት የጻፈችውና የምትተረጉመው እንጂ ቤተ ክርስቲያንን ያስገኘ አይደለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ለአዋልድ መጻሕፍት ወላጃቸው ነው፡፡ ይህንም በብዙ ማስረጃና አመክንዮ እንደሚከተለው እናያለን፤

፩. መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ የቤተ ክርስቲያንን ቀዳሚነት ይመሰክራል

የሚከተሉት ጥቅሶች ቅዱሳት መጻሕፍቱ ከመጻፋቸው በፊት ቤተ ክርስቲያን እንደነበረች በደንብ ያስረዳሉ፤

  • በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት፥ የእነርሱና የእኛ ጌታ የሆነውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም በየስፍራው ከሚጠሩት ሁሉ ጋር ቅዱሳን ለመሆን ለተጠሩት (፩ኛ ቆሮ. ፩፥፪)፡፡

አንድ መልእክት (ደብዳቤ) ሲጻፍ ሦስት አካላት መኖራቸውን መረዳት ተገቢ ነው – ላኪው፣ መልእክቱና ተቀባዩ፡፡ ላኪውና ተቀባዩ በሌሉበት መልእክቱ ሊጻፍ አይችልም፡፡ የመልእክቱ ላኪ ቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡ ተቀባይዋ ደግሞ በቆሮንቶስ አገር ያለች የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ከመልእክቱ ላኪውና ተቀባዩ የሚቀድሙ ከሆነ መልእክቱን ለመቀበል ቅዱስ ጳውሎስንና ቤተ ክርስቲያንን በቅድምና መቀበል ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ ይህን ሲያስረዳ ቅዱስ ጳውሎስ ገና መልእክቱን ለመጻፍ ሲጀምርና ለማን እንደሚጽፍ ሲገልጽ “በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን” ማለቱ እርሱ መልእክቱን ከመጻፉ በፊት የቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን እንደነበረች የሚያሳይ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ቀድማ መኖሯ ብቻ ሳይሆን ሰዎችን ስትቀድስም ነበር፡፡ በሌላ አገላለጽ ሰዎችን ለመቀደስ የግድ መጽሐፍ ቅዱስ ወይም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች የጻፈው መልእክት አላስፈለጋትም ነበር፡፡ ይህም ይታወቅ ዘንድ የመልእክቱ ባለቤት “በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት” በማለት ገለጸ፡፡ ይህን የመሰሉና ተመሳሳይ እውነትን የሚመሰክሩ ብዙ ጥቅሶችን ማንሣት ይቻላል፡፡

  • በእግዚአብሔር ፈቃድ የኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያ የሆነ ጳውሎስ ወንድሙም ጢሞቴዎስ፥ በአካይያ አገር ሁሉ ከሚኖሩ ቅዱሳን ሁሉ ጋር በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን፤” (፪ኛ ቆሮ. ፩፥፩)፡፡
  • “በኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታንም ባነሣው በእግዚአብሔር አብ ሐዋርያ የሆነ እንጂ ከሰዎች ወይም በሰው ያልሆነ ጳውሎስ ከእኔም ጋር ያሉት ወንድሞች ሁሉ፥ ወደ ገላትያ አብያተ ክርስቲያናት፤(ገላ. ፩፥፩)፡፡
  • ጳውሎስና ስልዋኖስ ጢሞቴዎስም፥ በእግዚአብሔር አብ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስም ወደምትሆን ወደ ተሰሎንቄ ሰዎች ቤተ ክርስቲያን፤ (፩ኛ ተሰ. ፩፥፩)፡፡
  • እንዲሁም የምታየውን በመጽሐፍ ጽፈሕ ወደ ኤፌሶንና ወደ ሰምርኔስ ወደ ጴርጋሞንም ወደ ትያጥሮንም ወደ ሰርዴስም ወደ ፊልድልፍያም ወደ ሎዶቅያም በእስያ ወዳሉት ወደ ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ላክ አለኝ” (ራእ. ፩፥፲፩)፡፡ ባለራእዩ ቅዱስ ዮሐንስም በተመሳሳይ ራእዩን ካየ በኋላ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት እንዲጽፍ ተገለጸለት፡፡ ይህም ከመጽሐፉ በፊት አብያተ ክርስቲያናቱ እንደነበሩ የሚያስረዳ ነው፡፡ ዮሐንስም ራእዩን በማየት ይከብር ዘንድ መጽሐፍ አላስፈለገውም ነበር፡፡

፪. አመክንዮአዊ ማረጋገጫ

ከመጻሕፍት ሁሉ ቀድሞ የተጻፈው መጽሐፈ ሄኖክ ነው፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ ከመጻፉ በፊት ሰው ከአንድ ሺሕ ዓመት በላይ ያለ መጽሐፍ ኖሯል፡፡ መጽሐፈ ኢዮብና አምስቱ የኦሪት መጻሕፍት ከዚያ በመቀጠል ተጻፉ፡፡ የነቢያት መጻሕፍት ሺሕ ዓመታት ዘግይተው ክርስቶስ ሊወለድ በመቶዎች የሚቈጠሩ ዓመታት ሲቀሩት ተጻፉ፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ለመጀመሪያዎቹ ዐርባ ዓመታት መጻሕፍት አልተጻፉም፡፡ ከዚያ በኋላም የማቴዎስ ወንጌልንና የያዕቆብ መልእክትን የመሰሉት ቀድመው ተጻፉ እንጂ አብዛኞቹ የተጻፉት እስከ ፸ ዓ.ም. ድረስ ቆይተው ነው፡፡ የሐዲሳት መጻሕፍት የተጻፉት ደግሞ በመጀመሪያው ምዕተ ዓመት መገባደጃ ነበር፡፡ ይህም የሚያስገነዝበው፡-

ሀ. ለጽድቅና ለድኅነት የሚያስፈልገው መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ቢሆን ኖሮ መጽሐፉ በአንዴ አልቆና ተጠቃሎ ከአዳም ጀምሮ ላሉት ሁሉ ካለመድሎ መሰጠት አልነበረበትምን? መጽሐፍ ያልተሰጣቸውስ “እኛ በኃጢአት የወደቅነው መጽሐፍ ቅዱስ ስላልነበረን ነው” ብለው ምክንያት እንዲያቀርቡ ዕድል አይፈጥርላቸውም ነበርን? አምልኮን በመጽሐፍ ቅዱስ ብቻ የምንገድበው ከሆነ ለሁሉም ሁሉንም መጻሕፍትን ባለ መስጠቱ የእግዚአብሔር ፈታሒነት ላይ ጥያቄ አያስነሣም ነበርን?

ለ. በጥንቱ ዘመን መጻሕፍት ለየተጻፉላቸው ሰዎች በጥቅል (Scroll) መልክ ይገኙ ነበር እንጂ አሁን እንዳለው ሁሉም በአንድነት ተጠርዘው በአንድ ሰው እጅ ማግኘት አይቻልም ነበር፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ አሁን ባለው መልኩ ተሰብስቦ በአንድነት መገኘት የቻለው የማተሚያ ማሽን ከተሠራና በወረቀት ማተም ከተጀመረ በኋላ ነው፡፡ ምዕራፍና ቊጥር ወጥቶለት ለንባብ አመቺ የሆነው ደግሞ ከዐሥራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን በኋላ ነው፡፡ በጥንቱ ዘመን እያንዳንዱ መጽሐፍ በየቦታው በጥቂት መጠን ብቻ ይገኝ ነበር፡፡ የሮሜ መልእክት የሚገኘው ሮማውያን ዘንድ፣ የቆሮንቶስ መልእክት ከቆሮንቶስ ሰዎች ዘንድ … ወዘተ እንጂ እንደዚህኛው ዘመን በአንድ ጊዜ ተባዝተው ሁሉም ዘንድ የሚገኙ አልነበረም፡፡ ለዐራት ሺሕ ዓመታት ያክል የተጻፉትን እነዚህን ቅዱሳት መጻሕፍት ከሐሰተኞቹ ለይታና በቀኖና ወስና “እነዚህን ተጠቀሙ” ያለችው ቤተ ክርስቲያን አይደለችምን?

ቤተ ክርስቲያን ይህን ባታደርግ እኛም ከመጽሐፍ ቅዱስ ፈጽሞ የማንገናኝ በሆንን ነበር፡፡ ወንጌላትን በጊዜው ብዙዎችን ያስቱ ከነበሩት “የይሁዳ ወንጌል”፣ “የበርናባስ ወንጌል” ከተባሉትና እነዚህን ከመሰሉት እንዲሁም “የማቴዎስ፣ የማርቆስ ወንጌል” ተብለው ብዙ ሐሰት ከተጨመሩባቸው ለይታ “መጻሕፍተ ወንጌላት ዐራቱ ብቻ ናቸው” ባትለን ኖሮ በብዙ ጥፋት ውስጥ የምንሆን አልነበርንምን? እርሷ በቀኖና ሰፍራ ቈጥራ የሰጠችውን መጽሐፍ ተቀብሎ ሰጪዋን ቤተ ክርስቲያንን አልቀበልም ማለትስ ስሕተት አይደለምን? በተመሳሳይ መልኩ ቀኖናን ሠርታ አዋልድ መጻሕፍትን ስትሰጥ አለመቀበልስ አለማወቅ አይደለምን?

ሐ. የቤተ ክርስቲያንን ከሁሉ በላይ መሆንና ፍጹም የሆነ ሥልጣኗን የምናውቅ አሥራው መጻፍት ተብለው የሚታወቁት መጻሕፍትን ሰብስቦ ሰማንያ አንድ ብቻ ናቸው ብሎ ማን ነገራችሁ? ብንባል “ቤተ ክርስቲያን” እንላለን፡፡ “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” የሚሉት ወገኖች ግን “መጽሐፍ ቅዱስን ‘ስልሳ ስድስት’ ያላችሁ ማነው” ቢባሉ ማን ይሉ ይሆን? እንቀበላቸዋለን የሚሏቸው “ስልሳ ስድስትቱ መጻሕፍት” ራሳቸው “ስልሳ ስድስት ብቻ” ወይም “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” አይሉምና፡፡

፫. መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉንም ነገር ጠቅልሎ አለመያዙን ያስረዳል

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ፤ (ዮሐ. ፳፥፴) በማለት ክርስቶስ ያደረጋቸው ሁሉ የተጻፉ እንዳልሆነ አስረድቷል፡፡ እንዲያውም እርሱ ያደረገውን ሁሉንም እንጻፍ ማለት እንደማይቻል ሲገልጽ ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል” ብሏል፡፡ ይህ መጽሐፍ ቅዱስ ሁሉንም ታሪክ፣ ሁሉንም ሥርዐት … ወዘተ ጠቅልሎ እንዳላካተተ የሚያሳይ ነው፡፡ ይህን ስንል ግን በጽሑፍ ደረጃ አልዘረዘረም ማለታችን እንጂ ከምሥጢር ምልዐት አንጻር የጎደለው ነገር አለው ማታችን አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሁሌም ምሉዕ ነውና የእግዚአብሔር ቃል የሚገኝበት መጽሐፍም ሕፀፅና ጉድለት የማይገኝበት ምሉዕ ነው፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስ ባነሣው ጉዳይ ላይ ተጨማሪ መንፈሳዊ ዕውቀት የምንፈልግ ከሆነ የቀረው ነገር የት እንደሚገኝ አዋልድ መጻሕፍትን ጠቁሞናል እንጂ “ሁሉንም ጠቅልዬ ይዣለሁና እኔን ብቻ አንብቡ” አላለም፡፡ የሚከተሉት አሳቦችም ይህንኑ የሚያስረዱ ናቸው፡፡

  • የቀረውም ፊተኛውና ኋለኛው የሰሎሞን ነገር በነቢዩ በናታን ታሪክ፥ በሴሎናዊውም በአሒያ ትንቢት፥ ስለ ናባጥም ልጅ ስለ ኢዮርብዓም ባየው በባለ ራእዩ በአዶ ራእይ የተጻፈ አይደለምን?” (፪ኛ ዜና. ፱፥፳፱)፡፡
  • የቀረውም የሮብዓም ነገር፥ ያደረገውም ሁሉ፥ በይሁዳ ነገሥታት ታሪክ መጽሐፍ የተጻፈ አይደለምን?” (፩ኛ ነገ. ፲፬፥፳፱)፡፡
  • “የቀረውም የሰሎሞን ነገር፥ ያደረገውም ሁሉ፥ ጥበቡም፥ እነሆ፥ በሰሎሞን ታሪክ መጽሐፍ ተጽፎአል (፩ኛ ነገ. ፲፩፥፵፩)፡፡

ማጠቃለያ

መጽሐፍ ቅዱስ የቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ ምንጭና ራስ ነው፡፡ ማንኛውም ትምህርት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ወይም ሥርዐት በመጽሐፍ ቅዱስ ከተጠቀሰው ጋር የሚጋጭ ከሆነ በቤተ የቤተ ክርስቲያናችን ተቀባይነት የለውም፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን የትምህርተ ሃይማኖት ዋና ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ የሥርዐትና የታሪክ ዋና ምንጭም መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን መጽሐፍ ቅዱስ የሚያዘውን የምትፈጽም፣ የምታስተምርና የምትኖር መጽሐፍ ቅዱሳዊት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስንም እንድናነበውና እንድንማርበት አዘጋጅታ የሰጠችን እርሷው ናት፡፡ ይሁንና አንዳንድ መናፍቃን መጽሐፍ ቅዱስን የሚከተሉ መስለው ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስን ያልሰበከች አስመስለው ስለሚያቀርቡ ተንኮላቸውን ተረድተን ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የማይለውን እንደሚል አድርገው በማቅረብና አጣመው በመተርጎም የሚስቱ ብዙዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው ከሁሉ የምትቀድመውን ቤተ ክርስቲያን እየተቃወሙ እርሷ ለዓለም ሁሉ የሰጠችውን ቅዱስ መጽሐፍ የተቀበሉ የሚያስመስሉት፡፡

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከሚዋጉአት ክፍሎች ተሐድሶ ፕሮቴስታንቶች ዋናዎቹ ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን ከሚያታልሉበት ፕሮቴስታንታዊ መንገድ አንዱ ደግሞ “መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” የሚለው አስተምህሮ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም አመክንዮም የማይደግፉትን ይህን የስሕተት መንገድ በመያዝ ቤተ ክርስቲያንን ይከሳሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ ቢሉም መጽሐፍ ቅዱስ የሚመሰክርላትን ልዕልናዋን አይቀበሉም፡፡ የመረጡትን ይወስዳሉ፤ ያልተስማማቸውን ይተዋሉ፡፡ አስቀድመን እንዳየነው አንድ አማኝ ቤተ ክርስቲያን ሁሉን የምትይዝና ከሁሉ ይልቅ የበለጠች መሆኗን መረዳት ይገባዋል፡፡ አንድ ጥያቄ ቢፈጠርበት እንኳን በቤተ ክርስቲያ ውስጥ ካለ አይቸገርም፡፡ ምክንያቱም ዛሬ ያላወቀውን ነገ ያውቃል፤ ዛሬ ያልተረዳውን በሕይወትም፣ ከአባቶች ጠይቆም ይረዳል፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ካላሳያችሁኝ የሚል አይሆንም፡፡ ይልቁንስ በመጽሐፍ ተጽፎ ያላገኘውን ከሁሉ ይልቅ ከፍ ካለችው ከቤተ ክርስቲያን ለማግኘት ይጥራል እንጂ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! ይህ ትምህርት፣ ከታኅሣሥ ፲፮ – ፴ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በታተመው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ በንቁ ዓምድ ሥር ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡