የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዝርወት ክፍል ሦስት

 

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

ባለፈው ዕትማችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ በዝርወት /ከኢትዮጵያ ውጪ/ ያደረገችውን ረዥም ሐዋርያዊ ጉዞ የሚዳስስ ጽሑፍ ማውጣታችን ይታወሳል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

1.1. ውስጣዊ ችግሮች

ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ የታሪክ ጉዞዋ ያጋጠሟት ችግሮች ወደ ኋላ ሲቃኙ በብዛት ከልዩ ልዩ አረማውያንና አላውያን ነገሥታት የመጡባት ውጫዊ ፈተናዎች በርከት ብለው ይታያሉ፡፡ እሷን ለመፈተን የማይታክተው ዲያብሎስ በዚህ ዘመን ደግሞ ከውጫዊው ፈተና ባልተናነሰ መልኩ አንዳንድ ክፍተቶችን በመግቢያነት እየተጠቀመ ቤተ ክርስቲያኗ በተለያዩ ውስጣዊ ችግሮች እንድትፈተን በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ እነዚህን ችግሮች አንድ በአንድ እንደሚከተለው እንዳስሳለን፡፡

ሀ. አስተዳደራዊ ችግር

በዝርወት ያለችዋ ቤተ ክርስቲያናችን በስደት ካሉ ልጆቿና አካባቢው ከሚፈጥረው ምቹ ሁኔታ ሊገኝ የሚችል ኃይሏን በአግባቡ ተጠቅማ አገልግሎቷን እንዳታጠናክር በተለይ ከ1958 ዓ.ም ጀምሮ የገጠማት የአስተዳደር መለያየት ዕንቅፋት ሆኖባታል፡፡ ዛሬ በምንገኝበት ሰፋ ሰፋ ባለ ሁኔታ ብንከፍለው በውጭው ዓለም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሦስት ዓይነት አስተዳደር አላት፡፡ የመጀመሪያው ቤተ ክርስቲያኗ በየአካባቢው ባቋቋመቻቸው አህጉረ ስብከት በኩል በማእከላዊው የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደር ታቅፎ /በእርግጥ ይህም ቢሆን ያለው አስተዳደራዊ ቁርኝት የሚያረካ አይደለም/ አገልግሎት የሚሰጠው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በሀገራችን ከተከሠተው የመንግሥት ለውጥ ጋር ተያይዞ ወደ ሰሜን አሜሪካ የተሰደዱትን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አራተኛ ፖትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን በመያዝ ዘግይተው እሳቸውን የተቀላቀሉት ሌሎች ብፁዓን አበው መሠረትነው ባሉት ስደተኛ ሲኖዶስ ሥር ያሉ አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡ ሦስተኛው ደግሞ ከሁለቱም አይደለንም ገለልተኛ ነን በማለት የተቀመጠው ክፍል ነው፡፡ ይህ የአስተዳደር ልዩነት ሌሎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየበረከቱ የመጡ ችግሮችን እየወለደ አንዲት ቤተ ክርስቲያን ተጠናክራ ሐዋርያዊ አገልግሎቷን እንዳትሰጥ ዕንቅፋት ሆኖባታል፡፡

ለ. የተቀመጠ ግብና ዓላማ አለመኖር

ዓለም ዛሬ በደረሰበት የአሠራር ደረጃ አንድ ተቋም በሰፊው መክሮና ተችቶ ያስቀመጣቸው ዓላማዎችና ግብ ሊኖረው ግድ ይላል፡፡ ምክንያቱም ተቋሙ የዕለትም ይሁን የዓመት እንቅስቃሴውን እየገመገመ የደከመውን የማጠናከር በጠነከረው የመቀጠል እርምጃ የሚወስደው አስቀድሞ ካስቀመጣቸው ዓላማዎችና ግብ አንጻር ነውና፡፡ ይህንን አጠቃላይ መርሕ በጥንቃቄ ተግባራዊ የሚያደርግ ሕዝብና መንግሥታት ባሉበት በውጭው ዓለም የምትንቀሳቀስ ቤተ ክርስቲያናችን ለምትሰጠው አገልግሎትና በሰው ዘንድም ይሁን በደሙ በመሠረታት ክርስቶስ ዘንድ ለሚጠበቅባት ሰማያዊ አገልግሎት መሪ የሚሆኑ በግልጽ የተቀመጡ ዓላማዎችና ግብ ሊኖራት ሲገባ እንቅስቃሴዎቿ ሁሉ በየጊዜው በሚፈጠሩ ሁኔታዎች መሠረትነት የሚመራ ሆኗል፡፡

ሐ. የአሠራር መመሪያ አለመኖር

አንድ ተቋም የቆመለትን ዓላማ ከግብ ለማድረስ እንዲችል ከሚያደርጉት መሠረታውያን ነገሮች አንዱ ግልጽና ለአሠራር የሚያመች አንድ መሠረታዊ መመሪያ መኖሩ ነው፡፡ ከዚህ መሠረታዊ መመሪያ በመነሣትም በየደረጃው እንዲያገለግሉ ሆነው የሚቀረጹ መመሪያዎች ሊኖሩት ያስፈልጋል፡፡ በእነዚህ መመሪያዎች አማካይነት ተቋሙ እየተንቀሳቀሰ ድካሙንና ጥንካሬዉን በየዕለቱ እየገመገመ ጉዞውን ይቀጥላል፡፡

በውጭው ዓለም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስጠት ከጀመረችበት ጊዜ ጀምሮ አገልግሎቷን በተቀላጠፈ መልኩ እንድትፈጽም የሚያስችላት የአገልግሎት ፖሊሲም ይሁን መመሪያ የላትም፡፡ ድንገት ከውስጥም ይሁን ከውጭ የሚመጡ የአገልግሎት አሳቦች ወዲያው በሚመነጩ ደግም ይሁኑ መጥፎ ዘዴዎች ይፈጸማሉ እንጂ ለዚህ ዓይነቱ አገልግሎት ቃለ ዐዋዲውን መሠረት በማድረግ ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጀችው የውጭ ሀገር አገልግሎት መመሪያ የለም፡፡ ለማዘጋጀትም ፍላጎቱ ያለ መስሎ አይታይም፡፡

መ. በዕቅድና ሪፖርት አለመመራት

በውጭው ዓለም ያለችዋ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን በሚመሩ ዕቅዶችና አፈጻጸሟን በሚገመግሙ ሪፖርቶች አትመራም፡፡ በእርግጥ ይህ ችግር የማእከላዊው የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደር ነፀብራቅ መስሎ ይታያል፡፡ ይሁን እንጂ ሁሉም በሥርዓት በሚመራበት ሀገር ካለች ቤተ ክርስቲያን ተመሳሳይ ኋላ ቀርነት አይጠበቅም፡፡

ሠ. ወደ ባዕዳኑ ለመድረስ ያለው ጥረት አናሳ መሆን

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባላት የተስተካከለ ትምህርተ ሃይማኖትና ሰማያዊ ሥርዓት ብዙዎች ባዕዳን ከማድነቅ አልፈው በጥምቀት የሥላሴን የጸጋ ልጅነት አግኝተው ወደሷ ለመጠቃለል ይማልላሉ፡፡ ነገር ግን በአንጻሩ በየደረጃው ያለው የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደር ይህንን ተረድቶ ለዘርፉ ትኩረት በመስጠት ሲንቀሳቀስ አይታይም፡፡

ረ. ራሷን ለሌሎች ያለማስተዋወቅ ችግር

ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ የታሪክ ዘመኗ በመንፈሳውያን ልጆቿ የዳበሩ በቃልም በመጣፍም እየተወረሱ የቆዩ ልዩ ልዩ የሥነ ዜማ፣ የሥነ ጽሑፍ፣ የሥነ ሕንፃ፣ የሥነ ፍልስፍና ወ.ዘ.ተ. ዕውቀቶች አሏት፡፡ እነዚህ ዕውቀቶች በመልክ በመልኩ እየሆኑ ለማያውቀው ዓለም ቢቀርቡ ቤተ ክርስቲያኗን በማስተዋወቅና ገንዘብም በማስገኘት በኩል ቀላል የማይባል ሚና ይጫወታሉ፡፡ ነገር ግን በውጭው ዓለም ምናልባት አልፎ አልፎ እዚህና እዚያ ሊጠቀሱ የሚችሉ እንቅስቃሴዎች ካልሆነ በስተቀር በተጠናከረ መልኩ ሲፈጸም አይታይም፡፡ ይህንን ተግባር በማከናወን በኩል ሰፊ ሚና ሊጫወቱ በሚችሉ ኢንተርኔት ሬድዮ ቴሌቪዥን ፓልቶክ በመሳሰሉት መገናኛ ብዙኃን ቤተ ክርስቲያናችን ከሌሎች ኋላ ብትሰለፍ እንጂ ለውድድር የምትደርስ አትመስልም፡፡

ሰ. በአካባቢው ተወልደው የሚያድጉ ሕጻናትን ለማስተማር የሚያገለግል ወጥ የሆነ ሥርዓተ ትምህርት አለመኖር ምእመናን በስደት ሕይወት የሚወልዷቸውን ልጆች የሀገራቸውን ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዐተ እምነት እንዲሁም ቋንቋ ባሕልና ታሪክ ተምረው ያድጉ ዘንድ ከቤተሰባቸው ቀጥሎ ሐላፊነት ያለባት ተቋም ቤተ ክርስቲያናችን ናት፡፡ ነገር ግን ይህንን ሐላፊነቷን እንድትወጣ የሚያስችላት ወጥ የሆነ ሥርዓተ ትምህርት የላትም፡፡

 

1.2. ውጫዊ ችግሮች

ሀ. የቦታ እጥረት

በአካባቢው ከሚገኙ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በንብረትነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሆነ ሕንፃ ያለው አንድም የለም፡፡ ምንም እንኳን አንዳንዶቹ ስጦታ ሊባል በሚችል ሁናቴ በሀገሩ ከሚኖሩ የእምነት ድርጅቶች ሕንፃ ያገኙ ቢሆንም እንደራሳቸው ቆጥረው ሊገለገሉበት አልቻሉም፡፡ በመሆኑም በአካባቢው የምትገኘዋ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የቦታ ችግር አለባት ብሎ ማጠቃለል ይቻላል፡፡

ለ. የመናፍቃን ጥቃት

ወቅታዊው የቤተ ክርስቲያናችን በመናፍቃን የመጠቃት ችግር በሀገር ቤት ብቻ የተወሰነ አይደለም፡፡ በልዩ ልዩ ችግር የተነሣ ሀገሩን ለቆ በስደት በአውሮፓ የሚገኘው ምእመንም በመናፍቃኑ ልዩ ልዩ ሴራ እየተነጠቀና እየተደናገረ ይገኛል፡፡ በጥናቱ ሒደት ለመረዳት እንደተቻለው መናፍቃኑ በእናት ቤተ ክርስቲያኑ ጉያ ያለውን ምእመን ለመንጠቅ ከሚጠቀሙባቸው ዘዴዎች ውስጥ የምእመናኑን የማኅበራዊ ሕይወት ጉድለት፥ ሕመም፥ የገንዘብ እጦት፥ ትዳር ወ.ዘ.ተ. የመሳሰሉትን መጠቀም ዋናው ነው፡፡ እርስ በርስ በመረዳዳት በኩል ደግሞ በእኛ ምእመናን ዘንድ ድካም ይታያል፡፡

ሐ. ወቅታዊው የሀገራችን የፖለቲካ ሁኔታ

ምእመኑ በወቅቱ ፖለቲካ ክፉኛ በመናወጡ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ ተፅዕኖ አሳድሯል፡፡ ቤተ ክርስቲያኗን በአንድም በሌላ መንገድ በወቅቱ ፖለቲካ እጇ እንዳለባት በመቁጠር ምእመኑ አባቶቹን እንዲርቅና እንዲያወግዝ፥ አባቶችም የምእመኑን ጥያቄ በወግ እንዳይሰሙ አድርጓቸዋል፡፡

መ. የባሕል ተፅዕኖ

በአካባቢው ላለችዋ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ ዕንቅፋት የሆነው ምእመናኑ በሚኖሩበት ሀገር ባሕልና ልማድ ተፅዕኖ ሥር መውደቃቸው ነው፡፡ ይህ ተፅዕኖ ደግሞ በምእመናኑ ብቻ የተወሰነ ሳይሆን በካህናቱም አካባቢ ይታያል፡፡

IV. መፍትሔዎች

የዚህ ጥናት ዓላማ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያሉባትን ችግሮች ዘርዝሮ የሚፈቱባቸውን የመፍትሔ አሳቦች ማቅረብ ነው፡፡ ለችግሮች መፍትሔ ይሆናሉ የሚባሉ ነጥቦች በዝርዝር ይቀርባሉ፡፡ አንዳንዶቹ የመፍትሔ ሐሳቦች የራሳቸው የሆኑ ዝርዝር የስልት ጥናቶች የሚያስፈልጋቸው ይመስላሉ፡፡

ሀ. በአኅጉሩ አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያኗ ምልዓተ ጉባኤ /ካህናትና ምእመናን/ ተወያይተው የሚያስቀምጧቸው ዓላማዎችና ግቦች ማዘጋጀት

በዚህ ጥናት ሒደት እንደታየው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዚህ አካባቢ ልታከናውናቸው የሚችሉ በርካታ ተግባራት አሉ፡፡ ተግባራቱን ለማከናወንም የተለያዩ አካላት ትምህርተ ሃይማ ኖቷን፣ ሥርዓተ እምነቷንና ትውፊቷን አክብረው አብረዋት ሊሠሩ እንደሚፈልጉ ታይቷል፡፡ በመሆኑም በአኅጉሩ ያለችዋ ቤተ ክርስቲያን አካባቢው የሚጠይቀውን አገልግሎት በስደት ላለው ምእመንም ሆነ በትክክለኛው ትምህርቷና ሰማያዊ ሥርዓቷ ተማርኮ ወደ ዕቅፏ ለመግባት በደጅ ቆሞ ለሚጠባበቀው መንፈሳዊ ድጋፍ መስጠት እንድትችል በመሪ አሳብነት የሚያገለግሉ ዓላማዎችና ግቦች በአስቸኳይ ልታስቀምጥ ይገባል፡፡ ለዚህም አኅጉሩ ውስጥ ያሉትን ካህናትና ምእመናን ያሳተፈ አንድ አጠቃላይ ጉባኤ ማድረግ ይገባል፡፡

 

ለ. የአካባቢውን ሁሉን ዐቀፍ ሁኔታ ያገናዘበ ዝርዝር መመሪያ ማዘጋጀት

ዓለም አቀፋዊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምዕራቡ ዓለም በስደት ያሉ ልጆቿንና የሚፈልጓትን ለማገልገል በሐዋርያዊ እግሮቿ ገስግሳ ከተሻገረች በርካታ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ይሁን እንጂ ማዕከላዊው የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር የቤተ ክርስቲያኗን በምዕራቡ ዓለም መስፋፋት አስፈላጊነት አምኖ ለተግባራዊነቱ ቢንቀሳቀስም እነዚህ አብያተ ክርስቲያናት ይተዳደሩባቸው ዘንድ የውጭውን ዓለም ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘቡ ልዩ ልዩ መመሪያዎችን አውጥቶ አልሰጠም፡፡ በሀገር ቤቱ የቤተ ክርስቲያን ይዞታ መሠረት የተዘጋጁ መመሪያዎች ባሕር ተሻግረው እንዲያገለግሉ ይጠብቃል፡፡ ይህ የተሳሳተ ግንዛቤ የሕግና ሥርዓት ምንጭ የሆነች ቤተ ክርስቲያንን ከሚመራ አካል የሚጠበቅ አይደለም፡፡ በመሆኑም ይህ አስፈላጊ ግን የተረሳ ሳይሆን ጨርሶ ያልታሰበ ጉዳይ በአስቸኳይ ትኩረት ተሰጥቶት በውጭው ዓለም ያለች ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን የምትፈጽምባቸው ዐቢይም ይሁን ዝርዝር መመሪያዎች ሊዘጋጁና በተግባር ሊውሉ ይገባል፡፡ ለዚህም የአኅጉረ ስብከቱ ጽ/ቤቶች በአስቸኳይ በአካባቢው ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ አጠቃላይ የአሠራር መመሪያ አርቅቆ ለውሳኔ የሚያቀርብ አንድ ኃይለ ግብር /Task Force/ ሊሰይሙ ያስፈልጋል፡፡ የዚህ መፍትሔ አሳብ ተግባራዊ መሆን ከታች ለሚዘረዘሩ አስተዳደራዊ የመፍትሔ አሳቦች እንደ መሠረት ሆኖ ሊያገለግል ይችላል፡፡

ሐ. አስተዳደራዊ አንድነትን መፍጠር

ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አሐቲ ከሚያሰኟት ነገሮች አንዱ ማዕከላዊ በሆነ አንድ መንፈሳዊ አስተዳደር መመራቷ ነው፡፡ በመሆኑም በማዕከላዊው የቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና በአውሮፓ ባለችው ቤተ ክርስቲያን መካከል የጸና ግንኙነት እንዲኖር ያስፈልጋል፡፡ ይህ ተግባራዊ ይሆን ዘንድም ከሁለቱም አካላት ከፍተኛ ተግባር ይጠበቃል፡፡ ማዕከላዊው አስተዳደር በውጪው ዓለም ያለችዋን ቤተ ክርስቲያን መምራት እንዳለበት ተገንዝቦ ሊንከባከባት የአገልግሎት መመሪያም ሊሰጣት ይገባል፡፡ በየወቅቱ በሚያደርጋቸው ልዩ ልዩ ጉባኤያት ጠንካራ ውክልና ኖሯት እንቅስቃሴዎቿ ሁሉ እየተገመገሙ የደከመውን በማጠናከር የጎደለውን በመሙላት አገልግሎቷን በተጠናከረ መልኩ እንድትቀጥል ማድረግ ይገባዋል፡፡ አልፎ አልፎ በሚያደርጋቸው አስተዳደራዊ እንቅስቃሴዎችም በዝርወት ያለችዋን ቤተ ክርስቲያን የሚያገለግሉና የሚመሩ አባቶችን እና ምእመናንን ቅር የሚያሰኙ ተግባራት መፈጸም የለበትም፡፡ የሚወስዳቸውን አስተዳደራዊ እርምጃዎች ሁሉ በውጪው ካሉ አባቶች ጋር እየተመካከረ ሊሆን ይገባል፡፡

በውጪ ያሉ አባቶችና ምእመናንም አሐቲ በምትሆን ቤተ ክርስቲያን ከማዕከላዊው አስተዳደር ጋር አንድ መሆናቸውን ከልባቸው ሊያውቁት ይገባል፡፡ በመሆኑም ከላይ ለሚመጡ ትእዛዞችና የማስተካከያ አሳቦች ተገዥዎች መሆን አለባቸው፡፡ እነሱም አንዳንድ ውሳኔ የሚያስፈልጋቸውን ጉዳዮች ወደ ላይ እየላኩ የማስወሰን ልምድ ሊያዳብሩ ይገባል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እንደየ ደረጃው ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጀምሮ ብፁዓን አበው ወደ አኅጉሩ እየሔዱ ምእመናንን እንዲባርኩና በመንፈሳዊ አባትነታቸው የምእመኑን ችግር በቅርብ እንዲያዩ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ከላይ ለተባሉትም ሆነ ላልተባሉት ጉዳዮች ተግባራዊነት እያንዳንዱን የግንኙነት እንቅስቃሴ በግልጽ የሚያመላክት አጠቃላይና ዝርዝር መመሪያ ሊዘጋጅ ያስፈልጋል፡፡ ይኽ ዐቢይ ጉዳይ በሁለቱም አካላት ትኩረት ተሰጥቶት በአስቸኳይ ካልተተገበረ በትንሹም ቢሆን ብቅ እያለ የሚመስለውና በአሜሪካ የሚሰማው የቤተ ክርስቲያን ፈተና በዚህም መምጣቱ የሚቀር አይኾንም፡፡

መ. የዕቅድንና ሪፖርትን ጥቅም አስመልክቶ የተለየ ግንዛቤ መፍጠር

እንኳን የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትን ያህል የተቀደሰ ተግባር የትኛውም ቀላል እንቅስቃሴ በዕቅድና በሪፖርት በሚመራበት በዚህ ዘመን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰማያዊ ተልእኮዋን ለማስፈጸም የሚረዷት ሁነኛ የሥራ ዕቅዶች አውጥታ የዕቅዶቹንም ተፈጻሚነት በየጊዜው ሪፖርት እያቀረበች አለመወያየቷ አሳፋሪ ነው፡፡ በጀርመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን በዓመት አንድ ጊዜ በምታደርገው ጉባኤ ዕቅዶችና ሪፖርቶች ሲቀርቡ ይታያሉ፡፡ ነገር ግን የሚቀርቡት ዕቅዶችም ይሁኑ ሪፖርቶች ቤተ ክርስቲያኗ በዝርወት ላለው ሕዝብ ማድረግ የሚገባትን ያገናዘቡ ሳይሆኑ በቢሮ ሥራ የሚያልቁ በአመዛኙ ገንዘብ ነክ የሆኑ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በመሆኑም ቤተ ክርስቲያኗ ልትንቀሳቀስባቸው የሚገቧትን ጉዳዮች በየጊዜው እያገናዘቡ የሚቀርቡ የአገልግሎት ዕቅዶች እየነደፈች ያንንም ለምእመናኗ በግልጽ እያሳወቀች ልትንቀሳቀስ ይገባል፡፡ የሚፈለጉት አገልግሎቶች በዕቅድነት እየተያዙ እንዲፈጸሙ አባቶችንም ሆነ ምእመናኑን የማንቃትና የማደራጀት ሥራ ሊሠራ ይገባል፡፡

ሠ. ከአስተዳደራዊ ጉዳዮች ነጻ የሆኑ ጉባኤያትን በማዘጋጀት አባቶች ስለሚሰጡት አገልግሎት እንዲወያዩና ልምድ እንዲለዋወጡ ማድረግ

በጀርመን የሚያገለግሉ ካህናት ልዩ ልዩ ዓመታዊ በዓላትን መሠረት እያደረጉ በዓሉን በሚያደርገው አጥቢያ እየተገናኙ ይወያያሉ፡፡ ነገር ግን በጥናቱ ሒደት እንደታየው ብዙ ጊዜ የሚወያዩት በጥቃቅን አስተዳደራዊ ጉዳዮች እንጂ ስለ አገልግሎታቸውና የመሳሰሉት ላይ አይደለም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሁሉም ካህናት የሚንቀሳቀሱት የሳምንቱን መጨረሻ የትራንስፖርት ቲኬት በመግዛት ስለሆነ በዓሉ ካለቀ በኋላ በሩጫ ወደየመጡበት ይመለሳሉ፡፡ በመሆኑም ካህናቱ ስለ አገልግሎታቸው የሚወያዩባቸውና አዳዲስ ሥልቶች የሚቀ ይሱባቸው ራሳቸውን የቻሉ ጉባኤያት ማዕከላዊ በሆኑ ቦታዎች ማዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ በእነዚህ ጉባኤያት አማካይነት በአገልግሎት ጉዟቸው ስላጋጠሟቸው ችግሮች ይወያያሉ፤ ምእመናኑን የበለጠ የሚያገለግሉባቸውን መንገዶች ይተልማሉ ወ.ዘ.ተ.

ረ. አካባቢ ተኮር የሆኑ ትምህርቶችን መስጠት

ሰዎች በምግባራቸው ጎልብተው በእምነታቸው እንዳይጸኑ ከሚያደርጓቸው ነገሮች አንዱ አካባቢያዊ ተጽእኖ ነው፡፡ ይህ እውነታ በአውሮፓ በሚኖሩ ምእመናን ሕይወት ላይ በግልጽ ይታያል፡፡ በመሆኑም ወጣቶችም ይሁኑ ታላላቆቹ ምእመናን በእምነታቸው እንዲጸኑ ችግራቸውን ያገናዘቡ ትምህርቶች በልዩ ልዩ መንገድ ሊሰጣቸው ያስፈልጋል፡፡ በዚህ ረገድ በዚሁ ተወልደው ለሚያድጉ ሕፃናት ልዩ ትኩረት ሊሰጥ ይገባል፡፡

ሰ. ከተለያዩ የእምነት ድርጅቶችና የመንግሥት አካላት ጋር በመነጋገር ቦታዎች የሚገኙበትን መንገድ መፈለግ

በተደጋጋሚ ሲገለጽ እንደተሰማው አውሮፓና አውሮፓውያን ብዙ ገንዘብ አፍስሰው የገነቧቸው የጸሎት ቤቶች የቀደመ አገልግሎት ተቀይሮ የልዩ ልዩ ሥጋዊ ተግባራት ማከናወኛዎች ሆነዋል፡፡ ያ ዕጣና ፈንታ ያልደረሳቸውም ተዘግተው ይገኛሉ፡፡ በመሆኑም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሀገሩን ሕጋዊ ሒደት ጠብቃ እነዚህን ቦታዎች ማግኘት እንድትችል መንቀሳቀስ ይገባታል፡፡

ቀ. ስለ መናፍቃን እንቅስቃሴ መግለጽ

ምእመናኑ ከመናፍቃኑ ቅሰጣ ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እንዲጠብቁ በልዩ ልዩ መንገዶች መናፍቃን የሚያደርጓቸውን እንቅስቃሴዎች በመግለጽ ግንዛቤ ማስጨበጥ ያስፈልጋል፡፡ በተመሳሳይም መናፍቃኑ ምእመናንን ለመንጠቅ የሚጠቀሙባቸውን እርዳታ መሰል ዘዴዎች በማጥናት በቤተ ክርስቲያን በኩል አገልግሎቱ እንዲሰጥ ማድረግ ይገባል፡፡

በ. የፖለቲካ አመለካከቶች ከቤተ ክርስቲያንና አካባቢዋ እንዲጠፉ ማድረግ

በምዕራቡ ዓለም ቤተ ክርስቲያናችን ካሉባት ችግሮች አንዱ የፖለቲካ ዓላማ ያላቸው ግለሰቦች ምእመንነታቸውን ተገን በማድረግ ወደ ቤተ ክርስቲያኗ ልዩ ልዩ አስተዳደራዊ መዋቅሮች በመግባት ቤተ ክርስቲያኗን የግል ዓላማቸው ማራመጃ ማድረጋቸው ነው፡፡ ይህ ድርጊት ምእመኑን ከእናት ቤተ ክርስቲያኑ ይለያል፡፡ በመሆኑም በቤተ ክርስቲያኗ በልዩ ልዩ መዋቅር ያሉትን ፖለቲካዊ አመለካከቶች ከቤተ ክርስቲያኗ እየነቀሉ የማውጣት ሥራ መሠራት አለበት፡፡ ይህንንም ለማድረግ ምእመናንን በግልጽ ስለጉዳዩ እያነሡ ማስተማር፣ አመለካከቱ ያላቸውን አባቶችም ይሁን ግለሰቦች መምከርና ማስመከር እንቢ ያሉትንም በምእመናን ትብብር ከቤተ ክርስቲያኗ ማኅበር እንዲለዩ ማድረግ መቻል ይኖርበታል፡፡

ተ. የገጽታ ግንባታ ሥራ መሥራት

ከላይ እንደቀረበው በአውሮፓ ያለው ምእመን በብዛት ለአባቶች ክብር አይሰጥም፡፡ ይህም ከቤተ ክርስቲያን ምስጢራት ሱታፌ እንዲርቅ አድርጎታል፡፡ በመሆኑም ምእመኑ ለአባቶቹ ፍቅር ባጣበት በዚህ ዘመን የአባቶችን ገጽታ የማድመቁና ጥብቅና የመቆሙ ሥራ በእጅጉ ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም ሰባክያንም ሆኑ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አባላት በአገልግሎታቸው ሒደት ከምእመናን ጋር በሚያደርጉት ግንኙነት ሁሉ ስለ ካህናት ማንነትና ስለ አገልግሎታቸው አስፈላጊነት መልካሙን በመግለጽ የሕዝብ ግንኙነት ሥራቸውን ሊሠሩ ግድ ይላል፡፡

ቸ. አካባቢውን ያገናዘቡ የቃለ እግዚአብሔር ማስተላለፊያ መንገዶችን መጠቀም

ዛሬ ዓለም በደረሰበት የቴክኖሎጂ ዕድገት ደረጃ ዕውቀትን በቀላል ወጪና የሰው ኃይል ከአንዱ የዓለም ጫፍ ወደ ሌላው ለማስተላለፍ የሚያስችሉ መንገዶች አሉ፡፡ ለምሳሌ መረጃ መረብ፣ የርቀት ትምህርት፣ ፓልቶክ፣ የቴሌፎን ጉባኤ፣ ሬድዮና ቴሌቪዥን በዋናነት ሊጠቀሱ የሚችሉት ናቸው፡፡ እነዚህ መገናኛ ዘዴዎች በስፋት አገልግሎት ላይ በሚውሉባቸው ሀገራት አገልግሎት የምትሰጥ ቤተ ክርስቲያናን ለዓላማዋ ማስፈጸሚያ መጠቀም የውዴታ ግዴታዋ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ በየዘርፉ የሠለጠኑ ምእመናንን መመልመልና ወደ አገልግሎቱ ማሰማራት ይጠበቅባታል፡፡

ነ. ራሷን የምታስተዋውቅባቸው ልዩ ልዩ መንገዶችን መቀየስ

በአካባቢው ቤተ ክርስቲያኗ ራሷን ለማስተዋወቅ ከላይ የተዘረዘሩትን መንገዶች ከመጠቀም በተጨማሪ ልዩ ልዩ ዐውደ ርእያትን፣ ሲምፖዝየሞችን፣ የባሕል ማስተዋወቂያ ዝግጅቶችን ወዘተ. ማዘጋጀት ትችላለች፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ

 

weyenute

በንብና ነብር የምትጠበቀው ሥዕለ ማርያም “ወይኑት”

 ኅዳር 10 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በእንዳለ ደምስስ

 

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታላላቅ ገዳማት መካከከል በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ውስጥ የሚገኙት የመርጡለ ማርያም እና ደብረ ወርቅ ገዳማት በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ፡፡ ሁለቱም ገዳማት ጥንት መሥዋዕተ ኦሪት ይከናወንባቸው የነበረና ታላላቅ ታሪካዊ ቅርሶችንም ለትውልድ በማስተላለፍ ረገድ ትልቁን ድርሻ ከያዙት ቅዱሳት መካናት መካከል ይመደባሉ፡፡

 

መስከረም 29 ቀን 2006 ዓ.ም. በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ማርቆስ ጥሪ መሠረት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሚመራና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚገኙበት የልዑካን ቡድን መርጡለ ማርያም ገዳም አዲስ ለሚሠራው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን የመሠረት ድንጋይ ለማኖር፤ እንዲሁም በደብረ ወርቅ ማርያም ገዳም የተገነባውን መንበረ ጵጵስና ለመመረቅና ለዘመናዊ ትምህርት ቤት ግንባታ የመሠረት ድንጋይ ለማኖር ከሄደው ልዑክ ጋር ተጉዣለሁ፡፡

በመርጡለ ማርያም ገዳም የነበረን ቆይታ አጭር በመሆኑ መረጃዎችን ለማሰባበሰብ የጊዜ እጥረት ስላጋጠመኝ አልተሳካልኝም፡፡ በደብረ ወርቅ ገዳም ቆይታዬ ከቋጠርኳቸው መረጃዎች መካከል ቅዱስ ሉቃስ ከሣላቸውና ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙት ቅዱሳት ሥዕላት መካከል በንብና ነብር የምትጠበቀው ሥዕለ ማርያም /ምስለ ፍቁር ወልዳ/ “ወይኑት” ስለተሰኘችው ሥዕል ጥቂት ላካፍላችሁ፡፡ ደብረ ወርቅ ማርያም ገዳምን ላስቀድም፡፡

 

ደብረ ወርቅ ማርያም ገዳም

ደብረ ወርቅ ማርያም ገዳም በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት በእናርጅና እናውጋ ወረዳ ከአዲስ አበባ 290 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ትገኛለች፡፡ የኦሪት መሥዋዕት ሲሰዋባቸው ከቆዩት ቅዱሳት መካናት አንዷ ናት፡፡ በተለይም ከ250-351 ዓ.ም. መሥዋዕተ ኦሪት ሲሰዋባት እንደቆየች የጽሑፍ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

 

የጎጃም አፈ ጉባኤ በነበረው ምሑረ ኦሪት ያዕቆብ አማካይነት መሥዋዕተ ኦሪት ሲሰዋባት የቆየ መሆኑን በገዳሟ የሚገኙ የኦሪት ሥርዓት ማከናወኛ የነበሩ እንደ መቅረዝ፤ ስንና ብርት የመሳሰሉ ቅርሶች ከመመስከራቸውም በላይ በገዳሟ ውስጥ የሚገኘው የቤተ ክርስቲያኗ የታሪክ መዝገብ ያስረዳል፡፡

 

weyenuteእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከወዳጇ ጋር ወደ ምድረ ግብፅ ስትሰደድ ካረፈችባቸው ቅዱሳት መካናት መካከል አንዷ ደብረ ወርቅ መሆኗንም በድርሳነ ኡራኤል ላይ ተጽፎ ይገኛል፡፡ በ4ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በኢትዮጵያ የነገሡት ወንድማማቾቹ አብርሃና አጽብሃ ክርስትናን እያስፋፉ ከቦታ ቦታ ይዘዋወሩ በነበረበት ወቅት መርጡለ ማርያምን አቅንተው ክርስትናን መሥርተው ወደ ደብረ ወርቅ በመምጣት ከምሁረ ኦሪት ያዕቆብ ጋር ተገናኝተዋል፡፡ ያዕቆብን ክርስትናን አስተምረው የአዲስ ኪዳን ሥርዓትን በመመሥረት “ያዕቆብ ኤጲስ ቆጶስ ዘኢየሩሳሌም ደብረ ወርቅ” ብለው ሾመውታል፡፡

 

አብርሃና አጽብሃ ደብረ ወርቅ ላይ ቤተ ክርስቲያን ሳይሠሩ ዐረፍተ ሞት ስለገታቸው በእግራቸው የተተካው ዐፄ አስፍሐ ያልዝ በ351 ዓ.ም. ወደ ደብረ ወርቅ በመምጣት ቤተ ክርስቲያኗን አሰርቷል፡፡ የደብረ ወርቅ ማርያም ገዳም በዮዲት ጉዲት በመቃጠሏ በ1372 ዓ.ም. በዐፄ ዳዊት የገንዘብ ድጋፍ አባ ሰርፀ ጴጥሮስ በተባሉ አባት አማካይነት በድጋሚ ተሠርታለች፡፡ ከጊዜ በኋላም ቤተ መቅደሷን ዐፄ ገላውዴዎስ በኖራና ድንጋይ ሲያሠሯት፤ ቅኔ ማኅሌቷ ደግሞ በስክ እንጨት ካለምንም ምሥማር በዐፄ ተክለ ጊዮርጊስ ተሠርታለች፤ በ1963 ዓ.ም. ዐፄ ኃይለ ሥላሴም አሳድሰዋታል፡፡

 

ቤተ ክርስቲያኗ 44 ቆመብዕሴ/አምድ/፤ የውጪና የውስጥ 11 በሮች፤ 36 መስኮቶች ሲኖሯት የግድግዳ ላይ ሥዕሎቹ ዐፄ ዮስጦስ /1704 ዓ.ም./፤ 1873 ዓ.ም. የንጉሥ ተክለ ሃይማኖት ልጅ የሆኑት ራስ ኃይሉ አስለውታል፡፡ በቤተ ክርስቲያኗ ዘመናዊ ሙዚየም ውስጥ በርካታ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርሶችም ይገኛሉ፡፡

 

“ወይኑት” ቅዱስ ሉቃስ የሣላት ሥዕለ ማርያም

ዐፄ ዳዊት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተሰቀለበት መስቀል ጋር ወደ ኢትዮጵያ ካመጧቸው የቅዱስ ሉቃስ ሥዕላት መካከል “ወይኑት” የተሠነችው ሥዕል አንዷ ስትሆን ዐፄ ዘርዓweyenute 2 ያዕቆብ ለደብረ ወርቅ ማርያም ገዳም አበርክተዋል፡፡ እስከ ዛሬ ድረስም ተጠብቃ ትገኛለች፡፡ በ1660ዎቹ ዓ.ም. በዐፄ አእላፍ ሰገድ /ፃድቁ ዮሐንስ/ ለወይኑት ማስቀመጫ እቃ ቤት ይሆን ዘንድ ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በድንጋይና በኖራ በማስገንባት ጣሪያውን የሣር ክዳን በማልበስ አሠርተውላታል፡፡ ፎቁ ላይ ትናንሽ 8 መስኮቶችም ይገኛሉ፡፡

 

ሥዕለ ሉቃስ “ወይኑት”ን የሚጠብቁ ነጫጭ ንቦች የሚገኙ ሲሆን ጥቋቁር ንቦቹ ደግሞ ከመስኮቶቹ እየወጡና እየገቡ መመልከት የተለመደ ነው፡፡ ንቦቹ ከሕንፃው መሠራት ጋር እንደገቡ የሚነገር ሲሆን ማሩ እስካሁንም ተቆርጦ አያውቅም፡፡ ወይኑት በዓመት ለሦስት ጊዜያት ሕዝቡን ለመባረክ ወደ ቤተ መቅደስ ትወሰዳለች፡፡ መስከረም 21፤ ጥር 21 እና ነሐሴ 16፡፡ ሥዕሏ ወደ ቤተ መቅደስ ሥትወሰድ ንቦቹ አጅበዋት የሚሄዱ ሲሆን ስትመለስም አብረዋት ይመለሳሉ፡፡ ንቦቹ ሕዝቡን የማይተናኮሉ እንደመሆናቸው በተንኮል ወይም ለሥርቆት የመጣ ሰው ካለ ግን እየነደፉ እንደሚያባርሩ ከዚህ በፊት ከተደረጉት ገቢረ ተዓምራት በመነሳት ይገለጻል፡፡

 

ወይኑትን የሚጠብቁ ከንቦቹ በተጨማሪ ነብሮችም በሕንፃው ጣሪያ ላይ ይገኛሉ፡፡ ቀን እዚያው ተኝተው የሚውሉ ሲሆን ምሽት ላይ ምግብ ፍለጋ እንደሚወጡ ይነገራል፡፡ በአካባቢው የሚገኙ በጎች ወደ ቤተ ክርስቲያኗ ቅጥር ከገቡ ከነብሮቹ ጋር እንደሚጫወቱና እንደማይተናኮሏቸው የዓይን እማኞች ያስረዳሉ፡፡

 

የዐፄ ዮሐንስ 4ኛ ወታደር ሥዕለ ሉቃስ /ወይኑትን/ ለመሥረቅ ሞክሮ ንቦቹ ነድፈው እንዳባረሩት፤ እንዲሁም ዐፄ ዮሐንስ ከደርቡሽ ጋር ባደረጉት ጦርነት ሥዕለ ማርያምን /ወይኑት/ ይዘው ለመዝመት ባደረጉት ጥረት ንቦቹ ወታደሮቻቸውን- በመንደፍ አስጥለዋታል፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዳልሆነ የተረዱት ዐፄ ዮሐንስ ሥዕሏን ወደነበረችበት መልሰው እንደዘመቱ የቤተ ክርስቲያኗ የታሪክ መዝገብ ያስረዳል፡፡ የፋሺስት ኢጣሊያ ጦር ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት የደብረ ወርቅ ማርያም ገዳምን ለመዝረፍ ዕቃ ቤቱን ሰብረው ለመግባት ያደረጉት ጥረት እንዳይሳካ በማድረግ ጠባቂ ንቦቹ ወታደሮቹን በመንደፍ እንዳባረሯቸው መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ 

 

ይቆየን

 

sidet2

ከስደት የመመለሱ ምሥጢር

 ኅዳር 5 ቀን 2006 ዓ.ም.

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ

እግዚአብሔር በሐዲስ ኪዳን ሊያደርገው ያሰበውን ነገረ ድኅነት አስቀድሞ በብሉይ ኪዳንና ቅድመ ብሉይ ኪዳን ለሕዝቡ በተለያየ መንገድ መግለጹን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክሩልናል ዕብ 1÷1:: ምክንያቱም ፈታሒነቱና መሐሪነቱ የማይነጣጠሉ በመሆናቸው ነው ይሏል፡፡ የሰው ልጆች በዚያ ዘመን እግዚአብሔር ፈታሒነቱን በተከፈላቸው የኃጢአት ደመዎዝ የተረዱ ሲሆን መሐሪነቱን ደግሞ በተለያየ ኅብረ አምሳል መግለጹ አልቀረም:: ከእነዚያ ብዙ ከምንላቸው ኅብረ አምሳላት አንዱ እንዲህ የሚለው ነው “በዚያም ወራት እንዲህ ሆነ፤ ሙሴ ጎበዝ መሆን በጀመረ ጊዜ ወንድሞቹን ሊጎበኛቸው ወደ ወንድሞቹ ወጣ የግብፅም ሰው የወንድሞቹን የዕብራውያንን ሰው ሲመታ ተመለከተ” ዘጸ.2÷11፡፡ በፈርዖን ቤተ መንግሥት ላደገው ለዚያ ሰው የተነገረለት ቃል በዕውነት አስደናቂ ነው፡፡ ዕድሜው በአባቶቻችን አነጋገር አርባ ዓመት ሆኖት የነበረው ይህ ሰው በጉብዝናው ወራት ወደ ወገኖቹ ሲመጣ ከተማው መከራ የበዛበት፤ ሕዝቡ ለቅሶና ዋይታ የጸናበት አስቸጋሪ ወቅት ሆኖ ነበር የጠበቀው፡፡ የሰው ልጆች ከአስገባሪዎቻቸው የተነሣ እስከ ጽርሐ አርያም ዘልቆ የሚሰማ ጩኸታቸውን አሰምተው የጮሁበት፤ እግዚአብሔርም የሰውን ጩኸት የሰማበት ጊዜ ነበር፡፡ በሌላ አነጋገር የመከራው ማለቂያ፤ የመጎብኘቱ ዘመን መግቢያ ነበር ማለት ነው፤ በመከራ ዘመን የሚጎበኝ ወዳጅ ታማኝ ወዳጅ ነውና፡፡

ይህ የመጎብኘት ወራት ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚመጣበት ወራት አምሳል መርገፍ የሚሆን ወቅት ነበር፡፡ በዚያኛው ወራት የተነሣው ጎበዝ በመከራ ውስጥ ለነበረው ሕዝብ የደረሰለላቸው በአርባኛው ዓመቱ ነበር፡፡ በዚህኛው ወራት የተነሣው ኢየሱስ ክርስቶከስም ለሕዝቡ የደረሰለት በአራተኛው ክፍለ ዘመን ነው (ዘመነ አበው፣ ዘመነ መሳፍንት፣ ዘመነ ነገሥት፣ ዘመነ ካህናት) እነዚህ አራት ክፍላተ አዝማናት በእውነት የሙሴን አርባ ዓመታት ይመስላሉ፡፡ የሙሴ አርባ ዓመታት በፈርዖን ቤተ መንግሥት ውስጥ በዝምታ ያለፉ ዓመታት ናቸው፡፡

እስከ አርባ ዓመት ድረስ ሙሴ ወደ ወገኖቹ ሳይወጣ ለምን ዘገየ? በፈርዖን ቤተ መንግሥት ውስጥ ያደገ ሰው ቢሆንም ቅሉ ፈረዖናዊ እንዳልሆነ ከእናቱ የሰማው ገና በልጅነት ዘመኑ አልነበረምን? ቢሆንም ግን ዘገየ፡፡ የፈርዖናውያን ግፍ እስኪፈጸም፤ የእስራኤልም መከራ እስኪደመደም አልጎበኛቸውም ነበር፡፡ ዛሬ የእስራኤል የመጎብኘት ወራት ከመድረሱም ባሻገር ሙሴ ጎበዝ በመሆኑ ግብፃዊውን ገድሎ እስራኤላዊውን ማዳን የሚችልበት ደረጃ ላይ ነው ያለው፤ ስለዚህም ወደ ወገኖቹ ወጣ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በዝምታ ያሳለፋቸው አራቱ ክፍላተ አዝማናትም ከዚህ ጋር ተመሳሳዮች ናቸው፡፡ የሰው ልጅ የቀኖና ጊዜውን እስኪያጠቃልል መንጸፈ ደይን ወድቆ ለዘመን ዘመናት ያለቀሰ ቢሆንም በአራቱም ክፍላተ አዝማናት የነበረው የእግዚአብሔር ዝምታ አንዳንዶችን “ኢሀሎኑ በዝ ሰማይ አምላከ እስራኤል አዶናይ፤ በዚህ ሰማይ እስራኤልን የሚጠብቅ ጌታ እግዚአብሔር የለምን?” ብለው በሰለለ ድምፅ እንዲናገሩ አድርጓቸዋል፡፡

የመጎብኘት ጊዜው ሲደርስ የዲያብሎስ ምክሩ እንዲፈርስ የእግዚአብሔር ልጅ በሥጋ ወደ ወገኖቹ መጣ፡፡ ይህ ወራት የአዳም ሥጋ ጎበዝ እየሆነ የመጣበት ወራት በመሆኑ በወገኖቹ ላይ የነበረውን ፍዳና መርገምን እንቢ ብሎ ያለ ኃጢአትና ያለ በደል ሆኖ ተፀነሰ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ የግብፃዊው ምሳሌ የሆነው ዲያብሎስ ጉድጓዱ ተማሰ፤ ወገኖቹን ሊጎበኛቸው በመጣው በዚያ ሰው በኩል የማይደፈረው ተደፈረ፤ ግብፃዊው ተቀበረ፡፡ ይህ ጎበዝ እየሆነ የመጣው የሙሴ ወገኖች የተስፋ ምልክት እንደነበረ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል መዳን ለተደረገለት ቅዱስ ሕዝብም እግዚአብሔር ወደ ወገኖቹ የመጣባት የመጀመሪያዋ ዕለተ ፅንስ ከሲዖል እስከዚህ ዓለም ለነበሩ ነፍሳት የፀሐይ ብርሃን ብልጭ ያለባት ዕለት ናት፡፡ ከዚህም የተነሣ የዓመተ ምሕረት መጀመሪያ አድርገን እንቆጥራታለን፡፡

ምንም እንኳን ሙሴ ግብፃዊውን ገድሎ ሊታደጋቸው የሚችል መሆኑን ያስመሰከረ ቢሆንም ወገኖቹ ግን በእልልታ የተቀበሉት አይደሉም፡፡ እርሱ ግን በእጁ መዳንን እንዲሰጣቸው የሚያምኑ ይመስለው ነበር ሐዋ.ሥራ.7÷25፡፡ እስራኤልን የመታደግ ሥራውን ግብፃዊውን በመግደል የጀመረው ያ ታላቁ ታዳጊያቸው ከሁለት ቀን በኋላ ባደረገው ወገኖቹን የመጎብኘት ሥራ ከወገኖቹ በጎ ነገርን ሊያስገኝለት አልቻለም፤ ከሀገር ወጥቶ እንዲሰደድ የሚያደርግ ክፉ ሀሳባቸውን ሰማ እንጂ፡፡ ከወገኖቹ ከንቱ ሀሳብ የተነሣ አርባ ዓመታትን ያለ ኃጢአትና በደሉ በስደት አሳለፈ የምድያምን ካህን በጎች እየጠበቀ በባዕድ ምድር ለረጅም ዘመን ተቅበዘበዘ፡፡ ከንጉሡ ቤት ወጥቶ ሲሄድ የንጉሡ የልጅ ልጅ መባልን እንደ መቀማት አልቆጠረውም ራሱን ዝቅ አድርጎ በምድያማውያን ምድር ለሚገጥመው የመስቀል መከራ እንኳን የታዘዘ ሆነ እንጂ፤ የግብፅ ጌታዋ ሙሴ እንደ ባሪያ ዝቅ ብሎ የበግ እረኛ ሆነ፡፡ እግዚአብሔር ግን ከቀደሙት መሳፍንት ሁሉ በላይ የሆነ ስምን ሰጠው በግብፅ ካለው ተድላ ደስታ ይልቅ ከወገኖቹ ጋር መከራ መቀበልን መርጧልና መከራ በተቀበለላቸው ወገኖቹ ላይ ሹም አድርጎ ደስ አሰኘው፡፡

sidet2የአባቶቹን ዕዳ ሊከፍል የመጣው ዳግማዊው ሙሴ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ዓለም ነቢያትን እንዳሳደደች እርሱንም እንዲሁ አደረገችበት፡፡ ሙሴ ግብፃዊውን በገደለውና ለእስራኤልም የመዳን ተስፋን ባሳየ በሁለተኛው ቀን ከሀገር አስወጥታ እንዳሳደደች፤ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን በሰው ልጆች ታሪክ ጉልህ ስፍራ የነበረውን ቁራኝነትን በማጥፋት ይቅርታውን አሐዱ ብሎ በጀመረበት በሁለተኛ ልደቱ ሲገለጥ በገዛ ወገኖቹ በካህናትና በነገሥታት ምክር ከሀገር ወጥቶ ተሰደደ፡፡ ሙሴ ወደ ወገኖቹ የመጣባት ሁለተኛይቱ ቀን፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም በሥጋ የመጣባት ሁለተኛይቱ ልደቱ ሲነጻጸሩ እጅግ ይገርማሉ፡፡ ስለ ወገን እንጂ ስለ ራስ መኖርን የሚያስንቁ ዕለታት! እንደዚያኛው ወራት በዚህም ወራት ስለ ሕዝቡ የሚቆረቆር ሌላ ሙሴ ለምድር ተወልዶላታል፡፡ እግዚአብሔርነቱን እንደ መቀማት ሳይቆጥረው የባሪያውን መልክ ይዞ ከሰማይ ወደ ምድር መጣ፡፡ በብዙ ሠራዊት ዘንድ ጌታ የሆነው እርሱ ከአብ ጋር ተካክሎ ሲኖር ሳለ በፈቃዱ ከክፉ ወገኖቹ መካከል ተለይቶ ወደ ምድረ አፍሪቃ ተሰደደ፡፡ ሙሴን የሕዝቡ መከራ ውል ብሎ እየታየው በፈርዖን ቤት በደስታ መኖርን እንደከለከለው ከሕዝቡ ጋርም ስለሕዝቡ መከራ መቀበልን እንዲመርጥ እንዳደረገው ኢየሱስ ክርስቶስንም በሕዝቡ የደረሰው ግፍ ከሰማይ ወደ ምድር አመጣው፤ ነፍሴ እስከ ሞት ድረስ እጅግ አዘነች እስኪል ድረስ አስጨነቀው ፡፡

ሙሴ ስለ ሕዝቡ ወደ ምድረ አፍሪቃ ወርዶ በግ ጠባቂነትን ሥራ አድርጎ ኖረ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም ራሱን የገለጠው በዚህ ስም እንደነበረ ቅዱስ ወንጌል ምስክርነትን ይሰጠናል “እኔ የበጎች እረኛ ነኝ” እንዲል ዮሐ10÷11፡፡ በእውነት እዚህ ላይ ያለውን የእግዚአብሔር ዐሳብ እስኪ በደንብ ተመልከቱት፡፡ ለአርባ ዓመታት ግብፃዊነትን ስሙ አድርጎ የፈርዖን የልጅ ልጅ መባልን ተቀብሎ ይኖር የነበረው ሰው ሙሴን አስነስቶ በጉብዝናው ወራት ወገኖቹን አስጎበኘው፡፡ ያንን ተከትሎ ግብፅን ለቆ እንዲወጣ አድርጎ ከሌሎች ዐርባ ዓመታት በኋላ ተመልሶ ወገኖቹን እንዲያድናቸው አደረገው፡፡ እግዚአብሔር ጥበበኛ አምላክ ነው፤ ያባቶቹን የያዕቆብንና የአስራ ሁለቱን አባቶች ስደት የሚመልስ ትውልድ አስነስቶ ከግብፅ በተገኘው ሰው ግብፅን በዘበዛት፡፡ ይህንንም በማድረጉ በዚህኛው ወራት ለኛ ሊያደርጋት ያሰባትን በጎ ነገር አስቀድሞ ነገረን፡፡ በዚያኛው ወራት ሕዝቡን የታደገው መሪ በግብፅ ምድር ተወልዶ በፈርዖን ቤት ያደገ ነው እንዳልን ሁሉ በዚህኛው ዘመን ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ሊያድናቸው የመጣው ኢየሱስ ክርስቶስም ከግብፃዊው ሰው ከአዳም የተገኘ ተገኝቶም ስለ ወገኖቹ የሚቆረቆር ሆነ፡፡ በአባ እንጦንስ አነጋገር ግብፃዊ ማለት ሥጋዊ ስሜቱን ብቻ የሚንከባከብ ሰው ስያሜ ነው፡፡ አባ እንጦንስ ወደ ገዳማቸው እንግዳ ሲመጣ ስለመጣው እንግዳ መረዳት ሲፈልጉ እንግዳውን ለሚቀበለው ደቀ መዝሙር የሚያቀርቡት ጥያቄ “ግብፃዊ ነው? ወይስ ኢየሩሳሌማዊ?” የሚል ነበር:: ሥጋዊው በግብፃዊ መንፈሳዊው በኢየሩሳሌም ይሰየማሉና፡፡

የሙሴ እናት በፈርዖናዊው የባርነት ወቅት ሳለች ሙሴን ወለደች ለሌላው ትውልድ መድኃኒት እንዲሆን ታስቦም ለሦስት ወራት ሸሸገችው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም የተወለደው ዓለም በዲያብሎስ ብርቱ የዐመጻ ውጊያ ውስጥ በነበረችበት ጊዜ ነበር፡፡ በተወለደበት ወቅት ብዙ ሕፃናት ለሞት የተዳረጉ ቢሆንም እርሱ ግን ለብዙዎቹ ለመዳናቸው፤ ለመነሣታቸው የተሾመ ነበርና እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ሶስት ዓመታትን ሸሸገችው፡፡ ከዚያም በኋላ በግብፃውያን መካከል አድጎ ለግብፃዊቷ ዓለም ይደርስ ዘንድ ስደትን ገንዘብ አደረገ የአባቱ ያዕቆብ እና የሌሎችም ቅዱሳን ስደት እንዲያበቃ ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰደደ፡፡ ሲሰደድ ከጥቂቶቹ በስተቀር ስደቱን ማን አወቀ? ሕዝቡን ሲያወጣ ግን በሁሉም ዘንድ የተገለጠ ነበር፡፡ ስደቱ ለዚህ ሁሉ ሕዝብ መዳን ምክንያት ይሆናል ብሎ ማን አሰበ? ግን ሆነ፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አፍሪቃ ምድር ተሰዶም እንደ ሙሴ በእግዚአብሔር መልአክ እስኪጠራ ድረስ በምድረ አፍሪቃ መቀመጥን መረጠ ዘጸ3÷4፤ማቴ2÷20፡፡ ለዚህም ነው በመነኮሳቱ መጽሐፍ “ንዑ ንርአዮ ለወልደ መንክራት” ተብሎ የተጻፈው፡፡ ሙሴ ከግብፅ አስማተኞች ጋር ባደረገው ክርክር አሸንፎ ሕዝቡን ይዞ በመኮብለል ከግብፅ ወጣ፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በግብፅ ያሉትን ገዳመ ሲሐትን፤ ገዳመ አስቄጥስን ባርኮ፤ በግብፃውያን የሚመሰሉ አጋንንትን አባሮ እስክንድርያን መንበር አደረጋት፡፡ ከዚያ እስከ ዛሬ ግብፅ ያፈራቻቸው ቅዱሳን ሁሉ የዚያ ስደት ውጤቶች ናቸው፡፡ በሙሴ ወደ ግብፅ መመለስ የሞቱትም በሕይወት ያሉትም እስራኤላውያን ወደ ተስፋይቱ ምድር እንደ ተመለሱ፤ አማናዊው ሙሴ ኢየሱስ ክርስቶስም በስደቱ ለሞቱትም በሕይወት ላሉትም አባቶቻችን ተስፋ እያደረጓት ሳያገኟት ከሩቅ እየተሳለሟት ወደ አለፏት ቅድስት ምድር መንግሥተ ሰማያት ለመመለሳቸው ምልክት ሆነ፡፡ የክርስቶስ ከኢየሩሳሌም ወደ ግብፅ መሄድ ከገነት ወደ ሲኦል ያለውን የሰው ልጆች ስደት የሚያመለክት ሲሆን፤ ከግብፅ ወደ ኢየሩሳሌም ያደረገው መመለስ ደግሞ ከሲኦል ወደ መንግሥተ ሰማያት ያደረግነውን የይቅርታ ጉዞ ያሳያል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ በሙሴ መታዘዝና ወደ ግብፅ መውረድ ሕገ ኦሪት በሙሴ ተመሠረተች፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ እስከ መስቀል የደረሰ መታዘዝ ወንጌል ተመሠረተች፡፡ ለሁሉም ግን መሠረቱ ስደት መሆኑን ልብ ይሏል ፡፡ በዚያኛው ወራት በሙሴ የተመሰረተችው ማኅበር በዚህኛው ወራት በኢየሱስ ክርስቶስ ለተመሰረተችው ማኅበር ምሳሌ ነበረች፡፡ አባቶቻችን ነቢያቱ የክርስቶስን ቤተ ክርስቲያን እንደ ስደተኛ ቆጥረው “ተመየጢ ተመየጢ ሱላማጢስ፤ ሱላማጢስ ሆይ ተመለሽ ተመለሽ” መኃ 7÷1 እያሉ ሊያዩአት ሲመኙ ነበሩ ጊዜው ሲደርስ የሄሮድስ ሞት የስደት ዘመኗን አሳለፈው፡፡ ሔሮድስ የዲያብሎስ ምሳሌ ሲሆን ዲያብሎስ በመስቀል ራስ ራሱን ተቀጥቅጦ ሲሞት ቤተ ክርስቲያን ግን መኖር ጀመረች፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ በጠላቶቿ ላይ ድልን እየተቀዳጀች፤ ጠላቶቿን አሳልፋ ባለ ማለፍ ጸንታ ትኖራለች፡፡

እመቤታችን የሄሮድስን ሞት ከሰማች በኋላ ቁስቋም ከሚባል ተራራ ላይ ሆና ደስታዋን አብረዋት መከራን ከተቀበሉት ከዮሴፍና ከሰሎሜ ጋር አከበረች፡፡ የቤተ ክርስቲያንም ደስታ የሚጀምረው በተራራ ላይ ነው፡፡ እመቤታችን ደብረ ቁስቋም ላይ ሆና ከአባቷ ዳዊት ጋር “ርኢክዎ ለኃጥእ አብየ ወተለዐለ ከመ አርዘ ሊባኖስ ወሶበ እገብዕ ኃጣዕክዎ፤ ኃጥእ ሔሮድስን ከፍ ከፍ ብሎ ተመለከትኩት ስመለስ ግን አጣሁት” መዝ 36÷35 ብላ ዘመረች፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ቀራንዮ ላይ ለዘመን ዘመናት ያስጨነቃት ዲያብሎስ ተወግዶላት የሞቱትንም በሕይወት ያሉትንም አንድ አድርጋ በደስታ ዘመረች፡፡ የዚያኛው ወራት ስደት ለቀደመው የእግዚአብሔር ሕዝብ ከግብፅ መውጣት፤ የዚህኛው ወራት ስደት ለአሁኑ የእግዚአብሔር ሕዝብ ከሲኦል መውጣት ፊታውራሪ ነው፡፡ ያኛው ሕዝብ በዚያኛው ስደት እንደተዋጀ ይሄኛው ሕዝብ ደግሞ በዚህኛው ስደት ተዋጀ፡፡ ምክንያቱም ስደቱ ስደታችንን ሲያመለክት መመለሱ መመለሳችንን ያሳያልና፡፡

 

የማይስማሙትን እንዲስማሙ አድርጎ ፈጠራቸው

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ

እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥረው ከሰባት እርስ በርሳቸው ከማይስማሙ ነገሮች ፈጥሮታል:: አራቱ ባሕርያት እግዚአብሔር በጥበቡ ካላስማማቸው በቀር መቼም የማይስማሙ ባላንጣዎች ናቸው፡፡ ምን አልባት ተስማምተው ከተገኙም በጽርሐ አርያም ባለው የእግዚአብሔር ማደሪያ ብቻ ሊሆን ይችላል፡፡ በዚያ ግን ባለጠጋው እግዚአብሔር የውኃ ጣራ፤ የእሳት ግድግዳ ያለው አዳራሽ ሠርቷል፤ ዓለም ከተፈጠረ እስከ ዛሬ ተስማምተው ይኖራሉ እንጂ አንዱ ባንዱ ላይ በክፋት ተነሳስቶ ውኃው እሳቱን አሙቆት፤ እሳቱም ውኃውን አጥፍቶት አያውቅም፡፡ ይህ ትዕግስታቸው በፍጥረት ሁሉ አንደበት ሠሪያቸውን እንዲመሰገን አድርጎታል::

በታች ባለው ምድራዊ ዓለምም ያለው ብቸኛው የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሰው ልጅ ነውና እነዚህ እርስ በእርስ የማይስማሙ መስተጻርራን ነገሮች ተስማምተው የሚኖሩበት ዓለም ሆኗል፡፡ እሳት ከውኃ፤ ነፋስ ከመሬት ጋር የሚያጣብቃቸውን የፍቅር ሰንሰለት የሰው አዕምሮ ተመራምሮ ሊደርስበት የማይችል ታላቅ ምሥጢር ነው፡፡ ግን እንዴት ይሆናል? ነፋስ መሬትን ሳይጠርገው፤ መሬትም ነፋስን ገድቦ ይዞ መላወሻ መንቀሳቀሻ ሳያሳጣው፤ ተስማምተው እንዲኖሩ ያደረገ እግዚአብሔር ታላቅ ነው፡፡ ውኃና እሳት ተቻችለው አንድ ቤት ውስጥ መኖር ችለዋል፤ የጥንት ጠላትነታቸውን በጥበበ እግዚአብሔር አስታራቂነት እርግፍ አድርገው ትተው ከሞት በቀር ማንም ላይለያቸው በቃል ኪዳን ተሳስረዋል፡፡

አሁን እሳት ውኃን በቁጣ ቃል አይናገረውም ውኃም በእሳት ፊት ሲደነግጥ አይታይም እንዲያው ሰው በሚባለው ዓለም ውስጥ በሰላም ይኖራሉ እንጂ፡፡ የነቢዩ ዳዊት ቃል ለነርሱ ያለፈ ታሪክ ማስታወሻ ቃል ነው፡፡ “ከመጸበል ዘይግህፎ ነፋስ እምገጸ ምድር፤ ከምድር ገጽ ላይ ነፋስ እንደሚበትነው አፈር…..” ይባል ነበር አባቶቻችንም ስለ ወንጌላዊው ማቴዎስ ሲተርኩልን “ሶቤሃኬ ተንሥአ ማቴዎስ ወንጌላዊ ከመ ተንሥኦተ ማይ ላዕለ እሳት፤ ውኃ በእሳት ላይ በጠላትነት እንዲነሣ ወንጌላዊው ማቴዎስም ተናዶ ተነሣ” በማለት ወንጌልን ለመጻፍ የተነሣበትን ምሥጢር አጫውተውናል፡፡ ማንኛውም ነገር አጥፊና ጠፊ ሆኖ ከተነሣ በእሳትና በውኃ መመሰል የተለመደ ጉዳይ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልዩ ሥነ ተፈጥሮ ባረፈበት የሰው ሕይወት ግን እንዲህ አይደለም፡፡ እሳትና ውኃ እስከ መቃብር የሚዘልቅ የፍቅር መንገድ ጀምረዋል ነፋስና መሬትም እስከ ፀኣተ ነፍስ ላይለያዩ ወስነዋል፡፡ ይህ የፍቅር ኑሯቸው ደግሞ ሌላ አዲስ ነገር ፈጠረላቸው ለመላእክት እንኳን ያልተደረገ አዲስ ነገር እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ላይ እንዲያደርግ አስገድዶታል፤ የማትሞትና የማትበሰብስ ነፍስን በሥጋ ውስጥ አኖራት፡፡ ሌላ አስደናቂ ነገር ነው፡፡ የአራቱ መስተጻርራን መዋሐድ የፈጠረው ሌላ አስደናቂ መዋሐድ፡፡

በጥቂቱም ቢሆን ከመላእክት ጋር ዝምድና ያላት ነፍስ በእጅጉ ከማይስማማት የሥጋ ባህርይ ጋር ተስማምታ መኖሯ አስደናቂ ነገር ነው፡፡ አራቱ ባህርያት ልዩነታቸውን አጥፍተው በፍቅር ተስማምተው ብታይ እሷም ሁሉን ረስታ ከሥጋ ጋር ተስማምታ ለመኖር ወሰነች እናም ሥጋ ብዙ ድካሞች እንዳሉበት ብታውቅም ከነድካሙ ታግሳው አብራው ትኖራለች፡፡ ሥጋ ይተኛል ያንቀለፋል፤ እሷ ግን በድካሙ ሳትነቅፈው እንዲያውም ተኝቶም በሕልም ሌሎችን የሕልም ዓለማት እንዲጎበኝ በተሰጣት ጸጋ ይዛው ትዞራለች፡፡ በሕልም ሠረገላ ተጭኖ በነፍስ መነጽርነት አነጣጥሮ የተመለከተውን አንዳንዱን ሲደርስበት ሌላውንም በሩቅ አይቶ ተሳልሞ ሲተወው ይኖራል፡፡

ያዕቆብ እንዳየው የተጻፈው ሕልም አስገራሚ ከሚባሉት ሕልሞች ዋናው ነው፡፡ ምክንያቱም በምድር ያለ ሰው የእግዚአብሔርን ዙፋን በሕልም ያየበትና የሰማይ መላእክትን የአገልግሎት ሕይወት የተካፈለበት ሕልም ስለሆነ ነው ዘፍ28÷10፡፡ ያዕቆብ በነፍሱ ያየው ይህ አስደናቂ ሕልም ከሦስት ሺህ የሚበዙ ዓመታትን አሳልፎ ፍጻሜውን በክርስቶስ ልደት አይተናል ዮሐ1÷50፡፡ ታዲያ ነፍሳችን በዘመን መጋረጃ የተጋረዱ ምሥጢራትን ሳይቀር አሾልካ መመልከት የምትችል ኃይል ናት ማለት ነው፤ እሷም የፍቅር ውጤት ናት፡፡ ተፈጥሮአችን ከምታስተምረን ነገሮች አንዱ ትዕግስት ነው፡፡ ሁልጊዜ ትዕግስት ፍቅርን፤ ፍቅር ደግሞ ሁሉን ሲገዛ ይኖራል ሰማያዊም ሆነ መሬታዊ ኃይል ለነዚህ ነገሮች ይሸነፋል ምን አልባት ሰው ሁሉን አሸንፎ የመኖሩ ምሥጢር ይህ ሊሆን ይችላል፡፡ ተፈጥሮው ትዕግስትን፤ ትግስት ደግሞ ፍቅርን ወልዳለታለች ከዚህ የተነሣ ተፈጥሮን መቆጣጠር የቻለ እንደሰው ያለ ማንም የለም፡፡ እስኪ ልብ በሉት ሞትን በቃሉ የሚገስጽ፣ ደመናትን በእጆቹ የሚጠቅስ፣ የሰማይን መስኮቶች የሚመልስ፤ እስከ ሰባተኛው ሰማይ ወጥቶ የሚቀድስ የሰው ልጅ አይደል? ባንድም ሆነ በሌላ መንገድ ሁሉም ነገር ለሰው አገልግሎት ሲባል የተፈጠረ ነው፡፡ የማይስማሙትን አስማምቶ ባንድ ላይ ማኖር መቻል ትልቅ ጥበብ ከመሆኑም በላይ ትዕግስት ካለ ሁሉም ፍጥረት ተቻችሎ ባንድነት መኖር እንደሚችልም አመላካች ነው፡፡

ተቻችለው የመኖራቸው ምሥጢር፡-
እያንዳንዳቸውን ብንመለከት አራቱም ባህርያት ለያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ባሕርያት አሏቸው፡- የእሳት ባህርይ ውእየትና /ማቃጠል/ ይብሰት /ደረቅነት/ ሲሆን፤ የውኃ ደግሞ ቆሪርነትና /ቀዝቃዛ/ ርጡብነት /ርጥብነት/ ናቸው፡፡ እነዚህ ሁለቱም ባህርያት በምንም ይሁን በምን መስማማት አይቻላቸውም እግዚአብሔር ግን በሌላ በኩል የእርቅ መንገድ ፈልጎ ሲያስታርቃቸው እንመለከታለን፡፡ ይሄውም በነፋስና በመሬት በኩል ነው፤ የነፋስ ባህርያት ውእየትና ቆሪርነት ሲሆን የመሬት ባህርያት ደግሞ ይቡስነትና ርጡብነት ናቸው፡፡ አሁን ዝምድናውንና ማንን በማን እንዳስታረቀ ስንመለከት እሳትና ውኃን በነፋስ አስታርቋቸዋል፡፡ ነፋስ በውዕየቱ ከእሳት፤ በቆሪርነቱ ከውኃ ጋር ተዘምዶ አለው፤ በመካከል ለሁለቱም ዘመድ ሆኖ በመገኘቱ እሳትን ከውኃ ጋር አንገቱን ደፍቶ እንዲኖር አድርጎታል፡፡ የመሐል ዳኛ ባይኖራቸው ኖሮ እሳቱ ውኃውን እንደ ክረምት ነጎድጓድ አስጩሆት ውኃውም እሳቱን እንደ መብረቅ ሳይታሰብ በላዩ ላይ ወርዶበት ተያይዘው በተላለቁ ነበር፡፡

ነፋስና መሬትን ደግሞ ውኃን ሽማግሌ አድርጎ ሲገላግላቸው እናያለን ውኃ በቀዝቃዛነቱ፤ ነፋስን በርጥበቱ መሬትን ይዘመዳቸዋል ይህን ዝምድናውን ተጠቅሞ ሁለቱን መስተጻርራን በትዕግስት አቻችሏቸው ይኖራል፡፡ አብረው በመኖራቸው ደግሞ ነፋስ ከመሬት ትእግስትን ተምሯል አብሮ መኖር ከሰይጣን ጋር ካልሆነ ከማንኛውም ፍጥረት ጋር ካወቁበት ጠቃሚ ነው፤ አብሮነት የለወጣቸው ህይወቶች ብዙ ናቸው፡፡ ዐስራ ሦስቱን ሽፍቶች ያስመነነው አንድ ቀን ከናፍርና ከሚስቱ ጋር የተደረገ ውሎ ነው፤ ያውም ገንዘብ ሊዘርፉና አስካፍን ሊማርኩ ሄደው ህይወታቸውን አስማረኩ፤ የጦር መሣሪያ ታጥቀው ሄደው ላልታጠቀው ተንበረከኩ፡፡ ክርስትና እንዲህ ሲሆን የእውነተኛነቱ ማረጋገጫ ነው ምክንያቱም ክርስትና ማለት አንዱ ብዙዎችን የሚያሸንፍበት፤ ወታደሩ ንጉሡን የሚማርክበት፤ ገረድ እመቤቷን የምታንበረክክበት ያሸናፊዎች ሕይወት ነውና፡፡ ሳይታኮሱ ደም ሳያፈሱ አብሮ በመዋል ብቻ ከህይወታቸው በሚወጣው የሕይወት መዓዛ ብቻ የሰውን አካሉን ብቻ ሳይሆን ልቡን ጭምር መማረክ ያስችላል፡፡ ዐስራ ሦስት ሰው ባንድ ጊዜ እጅ የሰጠውም ከዚህ የተነሣ ነው እናም አብሮነት የሚጎዳው ከሰይጣን ጋር ብቻ ከሆነ ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ግን የአትናስያን ሕይወት የለወጠ፤ ኃጢአቷን ከልቧ እንደ ሰም ያቀለጠ፤ ላንዲት ሰዓት ከዮሐንስ ሐጺር ጋር የነበራት ቆይታ ነው፡፡ እነ ማርያም ግብፃዊትን ከዘማዊነት ወደ ድንግልና ሕይወት የለወጠስ ላንድ ቀን ብቻ ወደ ኢየሩሳሌም ከሚሄዱ ሰዎች ጋር የተደረገ ውሎም አይደል? ያን የመሰለ የቅድስና ሕይወት ባንድ ጀንበር የገነባ አብሮነት በመሆኑ የሕይወት ትምህርት ቤት ነው፡፡

በእርግጥ እግዚአብሔር ያልባረካት ሕይወት ከማንም ጋር ብትውል ለውጥ እንደሌላት በይሁዳ፣ በዴማስ፣ በግያዝ ሕይወት ማወቅ ይቻላል፡፡ ይህ ማለት ግን የተሰበረ መንፈስ ለሌላቸው ቅንነት ለጎደለባቸው ማለት እንጅ አብሮ በመኖር የሚገኘውን ጥቅም የሚተካ ሌላ ነገር አለ ማለት አይደለም፡፡ ነፋስን በቅጽበት ዓለማትን መዞሩን ትቶ ባህሩን የብሱን መቆጣቱን ረስቶ ተረጋግቶ እንዲኖር ያደረገው ከመሬት ጋር አብሮ መኖሩ እኮ ነው ፡፡

መሬትም በአንጻሩ ከነፋስ ጋር በመኖሩ ፈጣን ደቀ መዝሙር ሆኗል፡፡ መሬትን የምናውቀው የማይንቀሳቀስ ፅኑ ፍጥረት መሆኑን እንጂ መሬት ሲንቀሳቀስ የምናውቀው አይደለምን? በሰው ባህርይ ውስጥ የመሬትን ባህርይ ተንቀሳቃሽ ያደረገው ከነፋስ ጋር አብሮ መሠራቱ ነው እንጂ ሌላ ምን አለው መጽሐፍ ስለ መሬት ሲናገር የተናገረው እንዲህ ነበር፡፡ ”ዘአጽንኣ ለምድር ዲበ ማይ፤ ምድርን በውኃ ላይ ያጸናት” መዝ 135÷6 በማለት የምድርን ፅናት ይመሰክራል፡፡ ሰውን ስንመለከተው ሌላ አዲስ ፍጥረት ይመስለን ይሆናል እንጂ በመጀመሪያ እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ሁለት ፍጡራን አንዷ ከሆነቸው ምድር የተገኘ ምድራዊ ፍጥረት ነው፡፡ ነገር ግን የሚንቀሳቀስ ምድር መሆኑ አስገራሚ ፍጥረት ያደርገዋል የዚህ ምሥጢር ደግሞ የተሠራበትን ምድር በነፋስ ሠረገላ ላይ ጭኖ የፈጠረው መሆኑ ነው የተጫነበት ሠረገላ ፈጣን ከመሆኑ የተነሣ የማይንቀሳቀሰውን እንዲንቀሳቀስ ያደርገዋል፡፡

መሬትም ለፈጣኑ የነፋስ እግሮች ጭምትነትን ያስተምርለታል፡፡ ባጭር ጊዜ አድማሳትን ማካለል የሚቻለው ነፋስ ጭምትነትን ገንዘብ ሲያደርግ ትዕግስትን ለብሶ ሲመላለስ ማየት ምንኛ ድንቅ ነው፡፡ ከዚያም በላይ አራቱንም በሌላ ሁለት ነገር እንከፍለዋለን፡- ቀሊልና ክቡድ ብለን፡፡ ቀሊላኑ እሳትና ነፋስ ሲሆኑ ክቡዳኑ መሬትና ውኃ ናቸው፡፡ እንደ ውኃና ነፋስ ምን ቀላል ነገር ይኖራል? እንደ መሬትና ውኃስ ማን ይከብዳል? ቢሆንም ግን አብረው ይኖራሉ እንዲያውም ክቡዳኑ መሬትና ውኃ ከላይ የተቀመጡ ሲሆን ቀሊላኑ እሳትና ነፋስ ግን ከስር ሆነው ክቡዳኑን ሊሸከሙ ከእግዚአብሔር ተወስኖባቸዋል፤ ሁለቱም እርስ በእርስ ተጠባብቀው ይኖራሉ፡፡ ነፋስና እሳት ቀላል ከመሆናቸው የተነሣ ወደ ላይ እንዳይወጡ መሬትና ውኃ ከላይ ሆነው ይጠብቃሉ፤ መሬትና ውኃ ደግሞ ከባዶቹ ናቸውና ወደታች እንውረድ ሲሉ ነፋስና እሳት ሓላፊነቱን ወስደው ከመውደቅ ይታደጓቸዋል፡፡ ይህ የተፈጥሮ ስጦታ ሰውን ወደታች ወርዶ እንጦርጦስ እንዳይገባ፤ ወደ ላይም ወጥቶ እንዳይታበይ ማእከላዊ ፍጡር አድርጎ ሲጠብቀው ይኖራል፡፡ ፈጡራንን ሲፈጥር በመካከላቸው መረዳዳትን የግድ ባያደርገው ኖሮ ማንኛውም ፍጡር አብሮ ለመኖር ባልተስማማ ነበር፡፡ ምንም ላንጠቅመው የሚወደንና የሚጠብቀን የሰማዩ አምላክ ብቻ ይሆናል፡፡ ፍጥረታት ግን እርስ በእርስ ተጠባብቀው የሚኖሩት አንዱ ያለ አንዱ መኖር ስለማይችል ብቻ ነው፡፡

እንደዚያማ ባይሆን ኖሮ ነፋስ እሳቱን አግለብልቦ አንድዶት እሳቱም በፋንታው ውኃውን አንተክትኮት ውኃም መሬትን ሰነጣጥቆ ጥሎት አልነበረምን? ግን ይህ ሁሉ ከመሆኑ አስቀድሞ ከእግዚአብሔር የተሰወረ አልነበረምና አራቱንም ኑሯቸውን እርስ በእርስ የተሳሰረ አድርጎታል፡፡ መሬትና በውስጧ የሚኖሩ አራቱ ባህርያት ተስማምተው መኖራቸው ከመሬት በላይ የሚኖሩ ፍጥረታት ተስማምተው እንዲኖሩ አድርጓቸዋል፡፡ አንዱ ሌላውን በመታገሱ የተከሰተ ነውና ለሁሉም ነገር መሠረቱ ትዕግስት መሆኑ የማይካድ ሀቅ ነው፡፡

ከዕለታት አንዳንድ ቀናት አሉ አራቱ ባህርያት የማይስማሙባቸው፡፡ ታዲያ በነዚህ ቀናት ሰው ተኝቶም እንኳን አይተኛም፤ የነፋስ ባህርይ የበረታ እንደሆነ ሲያስሮጠው ከቦታ ቦታ ሲያንከራትተው ያድራል፤ የመሬት ባህርይ ቢጸና ደግሞ ከገደል ሲጥለው፤ ተራራ ተንዶ ሲጫነው ያያል፤ እሳታዊ ባህርይም በእሳት ተከበን፤ እሳት ቤታችንን በልቶ ሲያስለቅሰን ያሳያል፤ ውኃም እንደሌሎቹ ሁሉ ሰውን በባህሩ ሲያጠልቀው ውኃ ለውኃ ሲያመላልሰው ያድራል፡፡ እያንዳንዳቸው ተስማምተው እንዲኖሩ ባያደርጋቸው ሰው በመኝታው እንኳን እረፍት ማግኘት እማይችል ፍጡር ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ትዕግስት ለማንኛውም ነገር መሠረት ነው፡፡

ሁሉም በጎ ነገሮች በሰማይም በምድርም የሚገኙት የትዕግስት ውጤቶች መሆናቸውን ልብ ይሏል፡፡ ሰው በራሱ የትዕግስት ውጤት መሆኑን ካየን የምንጠብቀው አዲሱ ዓለም መንግሥተ ሰማይ የትዕግስት ስጦታ ነው፤ ምክንያቱም መጽሐፍ የሚለው “እስከ መጨረሻው የታገሰ ይድናል” ነውና፡፡ ሞታችንን የገደለው፤ ጨለማን የሳቀየው ማነው? ክርስቶስ በዕለተ አርብ በህማሙ ወቅት ያሳየው ትእግስትም አይደል! ይሄ ትዕግስት ፍጥረቱን ሁሉ ያስደነቀ ትዕግስት ነበር፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት አንዱ “ኦ! ትዕግስት ዘኢከሠተ አፉሁ በሕማሙ በቅድመ እለ ይረግዝዎ፤ በመከራው ወቅት በሚወጉት ሰዎች ፊት የማይናገር ትዕግስት” ሲል በቅዳሴው ያደንቃል፡፡ በዚህ አስደናቂ ትዕግስቱ እኮ ነው ኃይለኛውን እስከ ወዲያው ጠርቆ ያሰረው ማቴ12÷29፡፡ ኃይለኛውን አስሮ ቤቱ ሲዖልን በርብሮ አወጣን፡፡ እንግዲያውስ ትዕግስት ጉልበት ነው፤ ትዕግስት ውበት ነው፡፡ በዓለም ላይ በጦርነት ከተሸነፉት በትዕግስት የተሸነፉት ይበዛሉ፤ ባለ መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ጦር የነበረው ሰናክሬም በሕዝቅያስ ትዕግስት መሸነፉን አንዘነጋውም፡፡

 

books 26

“አትሮንስ” የመጻሕፍት ውይይት መርሐ ግብር ሊጀመር ነው

 ጥቅምት 26 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በእንዳለ ደምስስ

books 26ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መጻሕፍት የንባብ ባሕልን ለማዳበር በየደረጃው ከሚሠራቸው ተግባራት በተጨማሪ “አትሮንስ” የተሰኘ በመጻሕፍት ላይ የሚደረግ የውይይት መርሐ ግብር ኅዳር 1 ቀን 2006 ዓ. ም. በማኅበሩ ኤዲቶሪያል ቦርድ አስተባባሪነት ይጀመራል፡፡

ንባብ ዕውቀትን ለማዳበር፤ አስተሳሰብን ለማስፋት፤ ሚዛናዊ ብያኔን ለመሥጠት፤ የአባቶችን ሕይወትና ትምህርት ለማወቅ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን የሚገልጸው የኤዲቶሪያል ቦርድ ክፍል፤ መንፈሳዊ መጻሕፍትን ማንበብ ዘላለማዊ ሕይወት ማግኛ መንገድን የሚጠርግና ጠቀሜታው የላቀ መሆኑን በመገንዘብ ተግባራዊ እንደሚደረግ አስታውቋል፡፡

የመርሐ ግብሩ ዋነኛ ዓላማም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከቱ የነገረ ሃይማኖት፤ የታሪክና የአስተዳደር መጻሕፍትን ማስተዋወቅ፤ የመንፈሳዊ መጻሕፍት የንባብ ባሕልን ማዳበር፤ በንባብ ባሕል ላይ የላቀ ልምድ ያላቸውን ሊቃውንት ልምዳቸውን እንዲያካፍሉ ማድረግ፤ በመንፈሳዊ መጻሕፍት ላይ የውይይት ባሕልን ማሳደግና የልምድ ልውውጥን ማጠናከር ላይ ትኩረት አድርጎ የተዘጋጀ መርሐ ግብር መሆኑን ከማኅበሩ ኤዲቶሪል ቦርድ ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

መርሐ ግብሩ ሳይቋረጥ እንዲቀጥል በኤዲቶሪያል ቦርድ የመጻሕፍት አርትዖት ክፍል ሥር ራሱን የቻለ ማስተባበሪያ ሆኖ እንደሚደራጅ የተገለጸ ሲሆን ዕቅድና ሪፖርት፤ አስፈላጊው በጀትም እንደሚኖረው ተጠቅሷል፡፡

“አትሮንስ” የመጻሕፍት ውይይት መርሐ ግብር ወር በገባ በመጀመሪያው እሑድ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት እስከ 11፡00 ሰዓት በማኅበሩ ሕንፃ ላይ በየወሩ እንደሚዘጋጅ ክፍሉ አስታውቋል፡፡ ኅዳር 1 ቀን 2006 ዓ.ም. በሚካሄደው መርሐ ግብርም “የኢትጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” የተሰኘውና በረዳት ፕሮፌሰር ሉሌ መላኩ የተጻፈው መጽሐፍ ውይይት ይካሄድበታል፡፡

ምእመናን በተጠቀሰው ቀን፤ ሰዓትና ቦታ በመገኘት መርሐ ግብሩን መከታተል እንደሚችሉም የማኅበረ ቅዱሳን የኤዲቶሪያል ቦርድ ክፍል ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

 

ትኩረት ለፊደላት

 

ጥቅምት 25 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በዳዊት ደስታ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለሀገራችን በርካታ ነገሮችን አበርክታለች፡፡ ከዚህም ካበረከተቻቸው ነገሮች ውስጥ አንዱ ኢትዮጵያ የራሷ ፊደል እንዲኖራት በማድረግ ነው፡፡ የቅርሳቅርስ ጥናት ሊቃውንትና ታሪክ ጸሐፊዎች እንደሚያረጋግጡት የአጻጻፍ ስልት በኢትዮጵያ የተጀመረው ከጌታ ልደት በፊት እንደነበር ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጭር የታሪክ የሃይማኖትና የሥርዐት መጽሐፍ ይገልጻል፡፡ /ገጽ. 9-11/

በአክሱም ዘመነ መንግሥት የሳባውያንና የአግዓዝያን ፊደላት በኅብረት ይሠራባቸው ነበር፡፡ በአክሱም ዘመነ መንግሥት ግን የግእዝ ፊደልና የግእዝ ቋንቋ እያደገ ስለመጣ በክርስቲያን ነገሥታት በአክሱም ዘመነ መንግሥት በሐውልቶችና በሌላም መዛግብት የተጻፉ ጽሑፎች በግእዝ ፊደልና በግእዝ ቋንቋ ተጽፈው እናገኛለን፡፡ የጽሑፍ መሠረት የሆነው ፊደልና የጽሑፍ ስልት በደንብ የታወቀው የክርስትና ሃይማኖት ማለት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት በኢትዮጵያ መስፋፋት በጀመረበት ወቅት መሆኑ ግልጽ ነው፡፡

የፊደል መነሻ
የግእዝ ፊደል መነሻ መልክእንና ቅርፅን በመስጠት እንዲስፋፋ ያደረጉት በአክሱም ዘመነ መንግሥት የነበሩ የቤተ ክርስቲያን /የቤተ ክህነት/ ሰዎች መሆናቸው የታመነ ነው፡፡ በሥነ ጽሑፍ የምትታወቀው ሀገራችን ኢትዮጵያ መሠረቷና መነሻዋ ፊደል ነው፡፡ ፊደል ያልተቀረፀለት ፣ጽሑፍ ያልተሰጠው ማንኛውም ቋንቋ ሁሉ መሠረት ስለሌለው የሚሰጠው አገልግሎት ያልተሟላ ነው፡፡ መሠረታዊ ቋንቋ ታሪካዊ ቋንቋ ተብሎ የሚሰየመው ፊደል ተቀርጾለት የምርምርና የሥነ ጽሑፍ መሠረት በመሆን ለትውልድ ሲተላለፍ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የታሪክ ማኅደር እንደመሆኗ ለግእዝና ለአማርኛ ቋንቋ መሠረትና መነሻ የሆነውን ፊደል ቅርጽና መልክ ሰጥታ ሕዝቡ እንዲጠቀምበት፣ ሥነ ጽሑፍ እንዲስፋፋና ታሪክ እንዲመዘገብ፣ ያለፈውን የማንነት አሻራ እንድናውቅ፣ አሁን ያለንበትን እንድንረዳና ወደፊት ስለሚሆነውም ዝግጅት እንድናደርግ በፊደል አማካኝነት ድርሳናትን ጽፈን እንጠቀም ዘንድ ፊደል መጠቀም ተጀመረ፡፡

ምክንያተ ጽሕፈት
ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ በመስከረም ወር ስለ ኢትዮጵያ ፊደል መሻሻል በሚዩዚክ ሜይዴይ አዘጋጅነት ለውይይት የሚረዳ መነሻ ጽሑፍ ቀርቦ ነበር፡፡ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ አማርኛ ፊደል ለመሻሻሉ መነሻ ያሉትን ምክንያትና የሌሎች ሀገራትን ተሞክሮ በማንሳት አሁን ያለው እየተገለገልንበት ያለው ፊደል ችግር አለው ያሉበትን ምክንያት አቅርበዋል፡፡ ፊደላቱ ተመሳሳይነት ድምጽ ስላላቸው ሊቀነሱ ይገባል በማለት ጽሑፋቸውን አቅርበዋል፡፡በዕለቱ የተለያዩ ምሑራን በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ስለነበር ጽሑፍ አቅራቢውን ሞግተዋቸዋል፡፡ የእኛም ዝግጅት ክፍል ፊደላት መቀነሳቸው/መሻሻላቸው/ የሚያመጣው ችግር ምን እንደሆነ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በመጠየቅ ምላሻቸውን አአስነብበናችሁ ነበር፡፡ ከዚህም በተለጨማሪ የቋንቋ ባለሙያዎች በእንደዚሁ ዓይነት የውይይት መድረኮች በመገኘት ምላሽ ሰጥተው በጽድፎቻቸውም በመጽሐፋቻቸውም ትክክለኛውን ለንባብ አብቅተውልናል፡፡

ይኼ ጽሑፍ የግእዝ ፊደል አመጣጥን የሚተርክ ሳይሆን ፊደላቱ ይሻሻሉ የተባለበትን መንገድ መሠረት አድርገን ምላሽ ብለን የምናስበውን የመፍትሔ ሐሳብ ለመጠቆም ነው፡፡ ተመሳሳይነት ያላቸውን ፊደላት ይቀነሱ፣ ይሻሻሉ…ወዘተ የሚሉ አሳቦች መቅረብ ከጀመሩ ቆይተዋል፡፡ ለዚህም እነ ዶ/ር ሐዲስ አለማየሁ “ፍቅር እስከ መቃብር” በሚል መጽሐፋቸው የተወጠነው፣ በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማእከል የተዋሀደው ፊደላትን የመቀነስ ዘመቻ በመጽሔቶችና ጋዜጦች ብቻ ሳይሆን በጥናታዊ ጽሑፎችና በፈጠራ ድርሰቶች ሳይቀር ይዞታውን እያስፋፋ እንደመጣ /ሊቀ ኅሩያን በላይ መኮንን ሥዩም፣ ትንሣኤ አማርኛ፣ ግእዝ መዝገበ ቃላት/ በሚለው መጽሐፋቸው ላይ ገልጸዋል፡፡

የዚህ ፊደል የማሻሻል ዘመቻ የፊደል ገበታችን አካል የሆኑት “ሀ፣ ሐ፣ ኀ፣ ሠ፣ሰ፣አ፣ዐ እና ጸ” ፊደላቱ ከትውልዱ አእምሮ ውስጥ መፋቅ /መጥፋት/አለባቸው የሚል አሳብ የያዘ ይመስላል፡፡ ይህን ዘመቻ በመቃወም ብዙ ሊቃውንት ብዕራቸውን አንስተዋል፣ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም በኅትመት ውጤቶቹ በሆኑት ሐመርና ስምዐ ጽድቅ ላይ የቋንቋ ምሁራንና የቤተ ክርስቲያናችንን ሊቃውንት በማናገር ምላሽ ብሎ ያሰበውን በተከታታይ ኅትመቶች አስነብቦናል፡፡

እነዚህ ፊደላት ተመሳሳይነት አላቸው የተባሉት የ“ሀ፣ ሐ፣ ኀ፤ ሠ፣ ሰ፤ አ፣ ዐ እና ጸ፣ ፀ” ፊደላት ቀደም ባለው ጊዜ በግእዝ፣ በተለይ ደግሞ በትግርኛ ቋንቋዎች የየራሳቸው መካነ ንባብና ድምፀት ስላላቸውና እልፍ አእላፋት የሥነ ጽሑፍ ሥራዎችም ስለተሠሩባቸው ፊደላቱን መቀነስ ኪሣራ እንጂ ትርፍ የለውም የሚል አስተያየት ከብዙ ምሁራን ተሰጥቶበጣል ፡፡

ከዚህ በመነሣት የፊደል ይቀነሱ፣ይሻሻሉ የሚሉት ጥያቄዎች ስናጤነው አንድን ፊደል በሌላ ፊደል ማጣፋት፣ ከቃላት ወይም ሐረጋት ፍቺ እንዲያጡ ወይም የተዛባ ፍቺ እንዲሰጡ ማድረጉ አይቀሬ ነው፡፡ ለዚህም አንድ ቀላል ምሳሌ ማንሳት እንችላለን፡፡ በግእዝ ቋንቋ “ሠረቀ” ማለት ወጣ፣ ታየ፣ ተገለጠ ማለት ሲሆን፣ “ሰረቀ” ማለት ደግሞ ሰረቀ፣ ቀጠፈ፣ አበላሸ ማለት ነው፡፡ የቃሉ ማእከላዊ ድምፅ “ረ” በሁለቱም አይጠብቀም፡፡ ጠብቆ ከተነበበ ስድብ ይሆናል፡፡ “ሠረቀ” የሚለውን ቃል የተወሰኑ ሰዎች ሲጠሩበት እናውቃለን፡፡ የአባት ስም ብርሃን፣ ፀሐይ ሕይወት ወዘተ ቢሆንና ሙሉ ስም አድርገን ስንጠራቸው ሠረቀ ብርሃን፣ ሠረቀ ፀሐይ፣ ሠረቀ ሕይወት እንላቸዋለን፡፡ ነገር ግን ንጉሡን “ሠ” በእሳቱ “ሰ” ቀይረን ብንጽፍ “ሌባው ብርሃን፣ ሌባው ፀሐይ. . .” እያልን የስድብ ቃል/ትርጉም/ ስለሚያመጣ ፊደላቱን አገባባቸውን የሚሰጡትን ትርጉም ካላወቅን ችግሮች ይፈጠራሉ፡፡

ሌላው ግእዝ “ሀ” በራብዕ “ሃ” አና “አ” በ”ኣ” መተካቱ ደግሞ “ሳይቸግር ጨው ብድር” የሚለውን የሀገራችንን አባባል የሚያስታውሰን ይመስለኛል፡፡ ሌላም እንመልከት ሀብታም ስንል ባለፀጋ ማለት ሲሆን ‹‹ሐብታም›› ካልን ደግሞ ዘማዊ ይሆናል፡፡ሰገል ጥበብ ማለት ሲሆን ሠገል ጥንቆላ ማለት ነው፡፡ ሰብዓ ፸ ቁጥር ሲሆን ሰብአ ሰዎች ማለት ነው፡፡ ሰአለ ለመነ ማለት ሲሆን ሠዓለ ሲሆን ደግሞ ሥዕል ሳለ ማለት ነው፡፡ ፊደላቱ አንዱ ባንዱ መቀየራቸው ወይም መተካታቸው ችግሮች እንደሚፈጥሩ ከላይ ያየነው ምሳሌ ጥሩ አድርጎ ያስረዳናል፡፡

ለዚህም አንዱ ከሌላው የሚሰጠውን የተለየ ትርጉም አለማወቅ የሚያመጣውን ችግርን አስመልክቶ ወጣቱ ገጣሚ ኤፍሬም ሥዩም “ሶልያና” በተሰኘው የግጥም የድምፅ መድብሉ በቅኔ መልክ ያቀረበውን ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ የግጥሙ ርእስ “እሳቱ ሰ” የሚል ነው፡፡

“ይኼው በጉብዝናም በፈቃድ ስተት
ትርጓሜው አይደለም አንድ ነው ማለት
እጽፋለሁ ጽፈት እስታለሁ ስተት
እሳት ስባል ንጉሥ፣ ንጉሥ ስባል እሳት”

እያለ ገጣሚው ፊደላት ያለ አገባባቸው ቢገቡ፣ የሚፈጥረውን የአሳብና የትርጉም ስሕተት እንደሚያመጣ ከፊደል ገበታ እንዲሠረዙ መደረጉ ያሳደረበትን የቁጭት ስሜት አሰምቶናል፡፡ ፊደላችን ይቀነስ፣ ይሻሻል የሚሉ አሳቦችን ከማንሳት በፊት ቀድሞ ሊነሣ የሚገባው ፊደላቱ የሚሰጡትን ድምጽና ትርጉም ማወቅ ከዚያም መቀነሳቸው ወይም መሻሻላቸው በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ የሚያመጣውን ተፅዕኖ ማየት ያስፈልጋል፡፡ከዚህም በተጨማሪ የታሪክና የቅርስ ማጥፋት ሥራ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ፊደላቱ የሚሰጡትን ድምጽና ትርጉም አውቆ የአንዱ ፊደል መውጣት መሻሻል ለረጅም ዘመናት የተጻፉ መጻሕፍት የአሳብ፣ የትርጉም፣ የቅርስ ጥፋት እንደሚያመጣ ማወቅ ይሻል፡፡ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ዳግም ጥያቄ በማያስነሳ መልኩ ትክክለኛውን ነገር ሊያስቀምጡና ጥናት በማጥናት ምላሻቸውን ሊሰጡ ይገባል፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ ባለድርሻ የሆነችው ቅደስት ቤተ ክርስትያን ምላሿን ማሳወቅ እንደሚገባት የጥያቄው መብዛት አፋጣኝ እንደሆነ ያመላክታል፡፡

 

ማእከሉ Tewahedo/ተዋሕዶ /የተሰኘ የስልክ አፕ አዘጋጀ

 

ጥቅምት 22 ቀን 2006 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

 

የማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ዘመኑን የዋጀ እንዲሆን Tewahedo /ተዋሕዶ የተሰኘ የስልክ አፕ/ በአይቲ ክፍል አዘጋጀ፡፡

 

በማእከሉ የተዘጋጀው አፕ የኢትዮጵያና የጎርጎሮሳዊያንን የዘመን አቆጣጠር አጣምሮ የያዘ ነው፡፡ የፈለጉትን ዓመት የበዓላት እና አጽዋማት ቀናት በቀላሉ ማየት ያስችላል፡፡ የየቀናቱን የቅዳሴ ምንባብ በመጽሐፈ ግጻዌ መሠረት ያሳያል፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥርዓት የጠበቁ መዝሙራት፣ ስብከቶች፣ ትረካዎች እና የሬዲዮ ስርጭቶች ለአድማጭ እንዲመቹ በዓይነት ከፋፍሎ ያቀርባል፡፡ አፑን በመጠቆም የቤተ ክርስቲያንን ድምጽ በየትኛውም ጊዜና ቦታ /በመንገድ ላይ ሥራዎችን እያከናወኑ፣ በእረፍትና በመዝናኛ ቦታዎች/ ሆነው በስልክ እነዚህን መረጃዎች እንደሚያገኙ ማእከሉ በላከልን መረጃ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

ሌላው በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መረጃ እንዲያገኙ የሚያግዝ ሲሆን በቀጣይ በሀገር ውስጥና በውጭ ላሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በቀላል መንገድ ቤተ ክርስቲያንን የሚያውቁበትና ትምህርቷን የሚከታተሉበት የቴክኖሎጂ ውጤቶች በስፋት እንደሚሠሩ ማእከሉ አሳውቋል፡፡