የኅዳር ጽዮን በዓል አከባበር ዛሬም ቀጥሎ በድምቀት ተከብሯል።

ዲ/ን አሉላ መብራቱና በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

ኅዳር 20 ቀን ከዋዜማው ጀምሮ መከበር የጀመረው የኅዳር ጽዮን በዓል ዛሬም ቀጥሎ በድምቀት ተከብሮ ውሏል።

ከትናንትና ማታ 2፡00 ደወል ከተደወለበት ጀምሮ፥ ሊቃውንት ካህናትና ዲያቆናት  ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በስብሐተ ማኅሌት በማድረስ ሌሊቱን አሳልፈዋል።

ሥርዓተ ማኅሌት እንዳለቀ ዛሬ ጠዋት 1፡00 ዑደተ ታቦት ተጀምሯል። ሁለት ዓይነት ዑደት የተካሄደ ሲሆን የመጀመሪያው ዑደት በሐውልት አደባባይ ተደርጓል። በዚያም የአክሱም ሊቃውንትና የሰ/ት/ቤት መዘምራን የክብረ በዓሉን ዝማሬ አቅርበዋል። በቦታው ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፥ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል።

ሁለተኛው ዑደት ቅዱስ ያሬድ የአርያም ዜማውን ባሰማበት በሙራደ ቃል ተከናውኗል። በዚህኛው ዑደት፥ ቅዱስነታቸው አቡነ ጳውሎስ ሠፋ ያለ ትምህርተ ወንጌል በሁለት ቋንቋ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ሰጥተዋል። የማዕከላዊ ትግራይ አክሱም ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሰላማ በዓሉን በተመለከተ አጠር ያለ መግለጫ ሠጥተዋል። በቅዱስነታቸው ጋባዥነት ብፁዕ አቡነ ኤልሣዕ ተጨማሪ ትምህርት ያስተማሩ ሲሆን የትግራይ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አባይ ወልዱ በበኩላቸው እለቱን አስመልክተው በንባብ ንግግር አሰምተዋል።

ሥርዓተ ቅዳሴ የተጀመረው ከቀኑ 6፡20 ነበር። በእለቱ ሠራየ ዲያቆን ሆኖ የቀደሱትና ከማኅበረ ቅዱሳን የአማርኛ መካነ ድር ጋር የስልክ ቆይታ ያደረጉት መ/ር ፍስሐ ጽዮን ደሞዝ እንደገለጹልን፥ በብፁዕ አቡነ ገሪማ፥ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስና በብፁዕ አቡነ ዲሜጥሮስ የተመራው የቅዳሴ ሥርዓት በ3 መንበር የተከናወነ ሲሆን፥ ሥርዓተ ቁርባኑ በእያንዳንዳቸው በ3 አቅጣጫ በአጠቃላይ በ9 ሙሉ ቀዳሽ ተከናውኗል። የቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ የጠጠር መጣያ ቦታ እስከሚታጣ ሙሉ ነበር።
እንደ መ/ር ፍስሐ ጽዮን ገለጻ፥ እርሳቸው በቀደሱበት በዋናው የእመቤታችን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የነበሩት መላው ምእመናን የቅዱስ ሥጋውና የክቡር ደሙ ተሳታፊ መሆናቸው ልዩ ድባብ ፈጥሯል። በአጠቃላይ ለምእመናን ቅዱስ ቁርባን ለማቀበል ብቻ ወደ አንድ ሰአት የሚጠጋ ክፍለ ጊዜ እንደወሰደ አያይዘው ገልጸውልናል።
ከዋዜማው ጀምሮ በ100,000ዎች ለሚገመቱ ምእመናን በአራቱም አቅጣጫ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሲስጥ ውሏል።  

/ከትናንት ጀምሮ መረጃዎችን ሲያደርሱን ለነበሩና ለተባበሩን ለንቡረ እድ በላይ መረሳ፣ ለመ/ር ፍስሐ ጽዮን ደሞዝና ለመ/ር ዲበኩሉ ልሳነ ወርቅ በእግዚአብሔር ስም ምስጋናችንን እያቀረብን ጥንቅራችን በዚህ እንቋጫለን/

        

አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል

በሰሙነ ሕማማት ጠቅለል ባለ መልኩ የምናስባቸው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማት አሥራ ሦስት ናቸው፡፡ እነርሱም አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል ይባላሉ፡፡ ለክርስቲያኖች እነዚህን ሕማማተ መስቀል ማወቅና ዘወትር ማሰብ ተገቢ በመሆኑ እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

1.     ተኰርዖተ ርእስ (ራስና በዘንግ መመታት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን በዘንግ መመታቱንና መቀጥቀጡን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተኰርዖት›› የሚለው ቃል ኩርዐ – መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ርእስ ደግሞ ራስ ማለት ነው፡፡ አገረ ገዥው ጲላጦስ ‹‹እኔ ከዚህ ጻድቅ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ›› ብሎ እጁን ከታጠበ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ገርፎ ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች አሳልፎ ሰጥቶት ነበር፡፡ በአይሁድ ሕግ የተገረፈ አይሰቀልም፤ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም፡፡ እርሱ ጲላጦስ ግን ከገረፈው በኋላ፣ የበደል በደል፣ እንዲሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው (ማቴ 27-24፤ ማር 15-15፤ ሉቃ 23-25፤ ዮሐ 18-39)፡፡
 
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተላልፎ ከተሰጠ በኋላ የእሾህ አክሊል ጐንጉነው ራሱ ላይ ደፍተውበታል፡፡ ራሱንም በዘንግ መትተውታል (ማር 15-19)፡፡ የሰው ዘር ከአዳም ጀምሮ በጠላቱ በዲያብሎስ በተጐነጐነ የኃጢአት እሾህ ራሱ ተይዞ ነበርና ይህንኑ ለማስወገድ ከሰማይ የወረደ ሰማያዊ የሆነ ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ ተንኮል የተጐነጐነ አክሊለ ሦክ እንደ ዘውድ ደፋ፡፡ በሲኦል ወድቆ በዲያብሎስ ተረግጦ ራሱ የሚቀጠቀጠውን የሰውን ልጅ ለማዳን መድኃኔዓለም ክርስቶስ ራሱን በመቃ ተቀጠቀጠ፡፡ ከራሱ ላይ በሚወርደው ደም ፊቱ ተሸፈነ፡፡
 
2.     ተፀፍዖ መልታሕት (በጥፊ መመታት)

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጃቸው በደም፣ ጣቶቻቸው በበደል በረከሰ በአይሁድ እጅ በጥፊ መመታቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተፀፍዖ›› የሚለው ቃል ፀፍዐ በጥፊ መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ መልታሕት ደግሞ ፊት ጉንጭ ማለት ነው፡፡
 
ጌታችን ለሊቀ ካህናት ቀያፋ እውነትን መናገር እንደ ስድብ ተቆጥሮበት መላልሰው ፊቱን በጥፊ መትተውታል፡፡ ፊቱንም በጨርቅ ሸፍነው ‹‹ክርስቶስ ሆይ በጥፊ የመታህ ማነው? ትንቢት ተናገርልን›› እያሉ ዘብተውበታል፡፡ በጠላት ዲያብሎስ እጅ ወድቆ በነፍሱ ይቀለድበትና ይንገላታ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ብሎ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ ወድቆ ተጐሰመ፤ ተንገላታ፤ በጥፊም ተመታ (ማቴ 27-27)፡፡ ጲላጦስ አሳልፎ ከሰጠው በኋላም አክሊለ ሦክ በራሱ ላይ አኑረው ቀይ ልብስ አልብሰው ‹‹የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን›› እያሉ እየተሳለቁበት በጥፊ መትተውታል (ዮሐ 19-2-4)፡፡ አላወቁትም እንጂ እርሱ በመንግሥቱ ሽረት፣ በባሕርዩ ሞት የሌለበት የዘለዓለም አምላክ ነው፡፡
 
3.     ወሪቀ ምራቅ (ምራቅ መተፋት)

ርኩሳን አይሁድ በብርሃናዊው የክርስቶስ ፊት ላይ በሚያስጸይፍ ሁኔታ ምራቃቸውን እንደተፉበት የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ወሪቅ›› የሚለው ቃል ወረቀ ካለው ግእዛዊ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ትርጉሙም እንትፍ አለ፣ (ተፋ) ማለት ነው፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ መጽሐፍ (ምዕራፍ 5ዐ-6) ‹‹ፊቴንም ከውርደትና ከትፋት አልመለስኩም›› ተብሎ እንደተነገረ እየዘበቱበት ምራቃቸውን ተፉበት (ማቴ 27-29-3ዐ፤ ማር 15-19)፡፡ በኃጢአት የቆሸሸውን የሰውን ሕይወት ለማጥራት የመጣው ንጹሐ ባሕርይ አምላክ ተተፋበት፡፡ በሥራው ከገነት ተተፍቶ፤ ተንቆ፤ ተዋርዶ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ኃጢአትን ይቅር የሚል እርሱ ጌታችን ያለ ኃጢአቱ ተተፋበት፤ ተናቀ፤ ተዋረደ፡፡ እንኳን በአምላክ ፊት በሰው ፊት እንኳን መትፋት እጅግ ያስነውራል፡፡ እርሱ ግን የኃጢአታችንን ነውር ከእኛ ሊያጠፋ ነውር የሆነውን ምራቅ ተቀበለ፡፡
 
4.     ሰትየ ሐሞት (መራራ ሐሞት መጠጣት)

ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ሳለ ተጠማሁ ባለ ጊዜ መራራ ሐሞት መጠጣቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ሰተየ›› ማለት ጠጣ ማለት ነው፡፡ ሐሞት የሚለውም አሞት ተብሎ በቁሙ ይተረጐማል፡፡ በመዝሙር 68 ቁጥር 21 ላይ ‹‹ለመብሌ ሐሞት ሰጡኝ፣ ለጥማቴም ሆምጣጤ አጠጡኝ›› ብሎ ነቢዩ ዳዊትን ትንቢት ያናገረ የነቢያት አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‹‹ተጠማሁ›› ባለ ጊዜ ሆምጣጤ ተሞልቶበት ተቀምጦ ከነበረው ዕቃ ሆምጣጤውን በሰፍነግ ሞልተው ወደ አፉ አቀረቡለት፡፡ ውኃ አጠጡኝ ቢላቸው በሐሞት የተደባለቀ የወይን ጠጅ ሊጠጣ አቀረቡለት፡፡ ቀምሶም ሊጠጣው አልወደደም (ማቴ 27-34)፡፡ ጌታችንም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ ‹‹ተፈጸመ›› አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ (ማቴ 27-48፤ ማር 15-36፤ ሉቃ 23-36፤ ዮሐ 19-29)፡፡
 
ቢጠጡት ለዘለዓለም የማያስጠማ ውኃ የሚሰጥ አምላክ፤ የተጠማችውን ነፍስ የሚያረካ ጌታ፤ ለዘለዓለም የሚፈልቅ የሕይወት ውኃ ምንጭ የሚያድል ፈጣሪ በተጠማ ጊዜ የፈጠረውን ውኃ እንኳን የሚያጠጣው የሚያቀምሰውም አላገኘም (ኢሳ 55-1)፡፡ አርባ ዓመት ሙሉ በቃዴስ በረሃ ኳትነው ለነበሩ አባቶቻቸው ከሰማይ መና አውርዶ የመገባቸው፤ ከአለት ላይ ውኃ አመንጭቶ ያጠጣቸው ክርስቶስ በተጠማ ጊዜ ቀዝቃዛ ውኃ ነፈጉት (ዘዳ 16-1-2ዐ፤ 1ቆሮ 1ዐ-3)፡፡ የዝናማት፤ የባሕርና የውቅያኖስ ጌታ በውኃ ጥም ተቃጠለ፡፡
 
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሲኦል በረሃ ወድቀው በሕይወት ውሃ ጥም የተቃጠሉትን ነፍሳት ለማርካት ሲል እርሱ ተጠማ፡፡ በኃጢአት ወድቀው፣ በበደል ረክሰው፣ በነፍሳቸው ተጐሳቁለው፣ መራራ መከራን የሚቀበሉትንና ምረረ ገሃነም አፉን ከፍቶ ሆዱን አስፍቶ የሚጠብቃቸውን ሁሉ ለማዳን መራራ ሐሞትን ቀመሰ፤ ሆምጣጣውንም ጠጣ፡፡ የመረረውን የሰው ልጆችን ሕይወት ለማጣፈጥ የመረረውን መጠጥ ተቀበለ፡፡

5.     ተቀሥፎ ዘባን (ጀርባን መገረፍ)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጀርባው እስኪላጥ ያለ ርኅራኄ የመገረፉን ነገር የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተቀሥፎ›› የሚለው ቃል ቀሠፈ- ገረፈ ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ‹‹ዘባን›› ደግሞ ጫንቃ፣ ትከሻ፣ ጀርባ ማለት ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጠው የተገረፈ አይሰቀልም፡፡ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም ነበር፡፡ ጲላጣስ ግን ኢየሱስ ክርስቶስን አስገረፈው፡፡ ከደሙ ንጹሕ ነኝ ብሎ ከታጠበ በኋላ ክርስቶስን ያለ ኃጢአቱ በመግረፍ ለአይሁድም አሳልፎ በመስጠት ‹‹ታጥቦ ጭቃ›› እንዲሉ የታጠበ እጁን መልሶ አቆሸሸው (ማቴ 27-28፤ ማር 15-15፤ ዮሐ19-1)፡፡
 
መድኃኒታችን መንፀፈ ደይን ወድቆ በእግረ አጋንንት ተጠቅጥቆ በእሳት አለንጋ የሚገረፈውን የሰው ልጅ ለማዳን ሲል ጀርባውን ለግርፋት ሰጠ፡፡ ሥጋው አልቆ አጥንቱ እስኪቆጠር ተገረፈ፡፡ አይሁድ አገረ ገዥያቸው ጲላጣስ ላቀረበላቸው ምርጫ ይፈታላቸው ዘንድ ነፍሳትን ከሲኦል የሚያወጣውን ክርስቶስን ሳይሆን ራሱን እንኳን ከምድራዊ ወህኒ ማውጣት ያልቻለውን ወንበዴውን በርባንን መረጡ፡፡ መገረፍ ይገባው የነበረ በርባን ተለቀቀ፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ ‹‹ጀርባዬን ለገራፊዎች፣ ጉንጬንም ለጠጉር ነጪዎች ሰጠሁ›› (በኢሳ 5ዐ-6) ተብሎ እንደተነገረ ጀርባውን ለገራፊዎች አሳልፎ ሰጠ፤ ጽሕሙንም ተነጨ፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው የሰው ልጅ ከሚያድነው አምላክ ይልቅ የሚገርፈውንና የሚዘርፈውን ወንበዴ መርጦ ስለተገኘ ነው፡፡
 
6.     ተዐርቆተ ልብስ (ከልብስ መራቆት)

አምላካችን ኢየሱስ ክርስስቶስ ልብሱን መራቆቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተዐርቆተ›› ማለት ታረዘ፤ ተራቆተ ማለት ነው፡፡ ፀሐይና ከዋክብትን ብርሃን አልብሶ የፈጠረ አምላክ ተራቆተ፡፡ ጸጋውን ለዕሩቃን የሚያለብስ አምላክ ልብሱን ተገፍፎ ዕራቁቱን ቆመ፡፡ ጨለማን ለብሶ ጨለማን ተንተርሶ ይኖር የነበረውን ሰው መልሶ ብርሃን ያለብሰው ዘንድ የብርሃናት ጌታ፣ የጸጋ ሁሉ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገፈፈ፤ ተራቆተ፡፡
 
የሲኦል ወታደሮች የሆኑት አጋንንት የሰውን ልጅ ጸጋ ገፍፈውት ነበርና ጲላጦስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አሳልፎ በሰጣቸው ሰዓት ወታደሮች ልብሱን ገፍፈውታል (ማቴ 27-27)፡፡ የሰው ልጅ ለቀረበለት ምርጫ የሰው ምላሽ ዘራፊው፤ ገራፊው ወንበዴ በርባን እንዲፈታለት ነበር፡፡ ‹‹አቅረብኩ ለከ እሳተ ወማየ፣ ደይ እዴከ ኅበ ዘፈቀድከ! እነሆ እሳትና ውኃን አቅርቤልሃለሁ፣ እጅህን ወደ ፈቀድከው ስደድ›› ሲባል የሰው ልጅ እጁን ወደ እሳት ሰደደ፡፡
 
7.     ርግዘተ ገቦ (ጎንን መወጋት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ጎኑን በስለታም ጦር መወጋቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ርግዘት›› የሚለው ቃል ረገዘ- ወጋ ከተሰኘ የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ ገቦ ማለት ደግሞ ጎን ማለት ነው፡፡ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ አጠገብ፣ በግራና በቀኙ ሁለት ወንበዴዎች ተሰቅለው ነበር፡፡ ሥጋቸው በሰንበት በመስቀል ላይ እንዳይኖር ጭናቸው ተሰብሮ እንዲወርዱ አይሁድ ጲላጦስን በለመኑት መሠረት ጭፍሮቹ የሁለቱን ወንበዴዎች ጭን ጭናቸውን ከሰበሩ በኋላ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ሲመጡ ፈጽሞ እንደሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፡፡ ነገር ግን ከጭፍሮቹ አንዱ ጎኑን በጦር ስለወጋው ወዲያው ከጎኑ ደምና ውኃ ፈሰሰ (ዮሐ 19-33)፡፡
 
አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ያደርገው ዘንድ ሞተ፤ የሰው ልጅ በዘለዓለማዊ ሞት ተይዞ ነበርና፡፡ ትልቁ ሞት በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር መለየት ነው፡፡ በጌታችን ሞት ግን ሞት ራሱ ድል ተነሣ፡፡ የሞት መውጊያ በሆነ ኃጢአት የሞተውን ሰው ለማዳን ጎኑን በጦር ተወጋ፡፡ በሰው ልቡና ተተክሎ የነበረውን ኃጢአት ከነሥሩ ነቅሎ ስለጣለው ‹‹ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ?›› ተባለ፡፡ የሞት መውጊያው ኃጢአት ነበርና (1ቆሮ 15-54-55፤ ኢሳ 25-8፤ ሆሴ 13-14)፡፡
 
ከተወጋው የጌታችን ጎን ደምና ውኃ መፍሰሱም የእግዚአብሔርን ልጅነትና የዘለዓለምን ሕይወት አጥቶ የነበረው ሰው ልጅነቱና ሕይወቱ እንደተመለሰለት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ምክንያቱም ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ተጠምቆ ልጅነትን፣ ደሙንም ጠጥቶ የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛልና (ዮሐ 3-5፤ ዮሐ 6-54)፡፡
 
8.     ተአሥሮተ ድኅሪት (ወደ ኋላ መታሠር)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት እጆቹን ወደኋላ የፊጥኝ መታሠሩን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተአሥሮት›› የሚለው ቃል አሠረ (ሲነበብ ይላላል) ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም አሠረ ማለት ነው፡፡ ‹‹ድኅሪት›› የሚለው ቃል ደግሞ ተድኅረ- ወደኋላ አለ ከሚለው ግሥ የወጣ ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጊዜው በደረሰ ሰዓት ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ በሰጠባት በዚያች ዕለትና ሰዓት ሻለቃውና ጭፍሮቹ የአይሁድም ሎሌዎች እጁን የኋሊት አሥረው መሬት ለመሬት ጎትተውታል፡፡ አፍገምግመውታል (ዮሐ 18-12)፡፡
 
በኃጢአት ሰንሰለት የኋሊት ታሥሮ ጠላት ዲያብሎስ የሚያፍገመግመውን የሰው ልጅ ለማዳን፣ ሰውንም ከኃጢአት እሥራት ይፈታ ዘንድ ሲል መድኃኔዓለም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ የኋሊት ታሠረ፡፡
 
9.     አምሥቱ ቅንዋተ መስቀል

መድኃኒታችን በመስቀል ላይ የተቸነከረባቸውን ጠንካራ የብረት ችንካሮች (ምስማሮች) የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ቅንዋት›› የሚለው ቃል ቀነወ- ቸነከረ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ መስቀል ማለት ደግሞ ዝም ብሎ የቆመ ግንድ ሳይሆን አሁን በየሥፍራው እንደምናየው ምልክት የተመሳቀለ እንጨት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቸነከረባቸው አምስቱ ችንካሮች ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፤ ሮዳስ ይባላሉ፡፡ እነዚህም የአምሥቱ አዕማደ ምሥጢራት ምሳሌዎች መሆናቸውን አበው ያስተምራሉ፡፡
 
ሐዋርያው ቶማስ ከትንሣኤ በኋላ ወንድሞቹ ሐዋርያት ስለ ትንሣኤው በነገሩት ጊዜ ‹‹የችንካሩን ምልክት በዓይኖቼ ካላየእንኳን ብንሆን እግዚአብሔር ከኛ ጋር ከሆነ ማንም አያሸንፈንም፡፡ 

የቤተክርስቲያን ፈተና እና ምዕመናን

በዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

መግቢያ

የቤተክርስቲያን ታሪክ የሚጀምረው ከዓለመ መላእክት ነው፡፡ ታዲያ ፈተና ሁሌ አብሯት የሚኖር ቤተክርስቲያን መፈተን የጀመረችው በዚሁ በዓለመ መላእክት ነበር፡፡ ዲያብሎስ ትዕቢትንና ሐሰት ከራሱ አንቅቶ መላእክትን «እኔ ፈጠርኋችሁ» በማለት ባሰማው የሐሰት አዋጅ ከሰው ልጅ ወደዚህ ምድር መምጣት ጀምሮ በብሉይ ኪዳንም በርካታ ፈተናዎች ተፈራርቀዋል፡፡

በብሉይ ኪዳን በብዙ ኅብረ ምሳሌ ከአቤል እስከ ክርስቶስ ምጽዓት ስትታሰብ የመጣች ቤተክርስቲያን በሐዲስ ኪዳን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ለማዳን በመጣ ጊዜ በአማናዊ ደሙ አጽንቶ አካለ ክርስቶስ አድርጓታል፡፡ /ኤፌ 1፥23/ ቤተክርስቲያን ለሰው ዘር ሁሉ በሰማይ ያለውን የእግዚአብሔርን መንግሥት የምታስተምር ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝበትና ወደ ሰማያዊው ርስትም የምትመራ የጽድቅ መንገድ ናት፡፡ መቼም ቢሆን ደግ ነገር ሁሉ የሚገጥመው ፈተና አይጠፋምና ቤተክርስቲያን ጉዞዋ ሁሉ በፈተና የታጠረ ነው፡፡

በዚህች አጭር ጽሑፍ ቤተክርስቲያን ፈተና በሚያጋጥማት ወቅት ምእመናን ምን ዓይነት ኑሮ መኖር፤ ምን ዓይነት አቋም መያዝ እንዳለባቸው ለማየት እንሞክራለን፡፡ ካሰብነው ለመድረስም ዋና ዋና የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጮችንና ያስከተሏቸውን ጉዳቶች ለማንሳት እንጀምራለን፡፡
1.    ዋና ዋና የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጮች
የቤተክርስቲያንን ታሪክ ስናጠና ለቤተክርስቲያን የመፈተን ምክንያት የሚሆኑ አካላትንና ድርጊቶችን ቆጥሮና ወስኖ ማስቀመጥ ወይም መገደብ ባይቻልም ጐልተው የሚታዩትን መዘርዘር ግን ይቻላል፡፡ ከእነዚህ የፈተና ምንጮች ዋነኞቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡
1.1 መናፍቃን
«የቤተክርስቲያን የውስጥ ጠላቶች በጌታ አነጋገር «ጸራዊ» በሐዋርያት አነጋገር «ቢጽ ሐሳውያን» በሊቃውንት አነጋገር «መናፍቃን» ይባላሉ፡፡ የቤተክርስቲያን ልጆች ሳይሆኑ የቤተክርስቲያን ልጆች መስለው ወይም ከቤተክርስቲያን እምነትና ትምህርት የተወሰነውን የተማሩ ፤የተወሰነውንም ተምረው ያልያዙ ጐደሎዎች ናቸው፡፡ እነርሱም እንክርዳድ ስንዴ መስሎ እንደሚያድግ በክርስቶስ ዐጸደ ወይን በቤተክርስቲያን ውስጥ የበቀሉ አሳሳቾች ናቸው፡፡ » /የቤተክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ ገጽ 48/
ብፁዕ አባታችን ከላይ እንደገለጹት እነዚህ ወገኖች ስልታቸውን በየስፍራውና በየዘመኑ እየለዋወጡ ሐመረ ኖኅ ቤተክርስቲያንን በምንፍቅና ማዕበላቸው እያንገላቷትና እያማቷት ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ወዳልተሰበኩት ሕዝብ ደርሳ ትምህርቷን እንዳታስተምር ልዩ  ልዩ የክህደት ትምህርት በመፍጠር አባቶችን ሥራ ያስፈቱ ናቸው፡፡ይልቁንም በአሁኑ ዘመን በክህደት ትምህርታቸው ብቻ ሳይቆጠቡ ቤተክርስቲያን ላይ ሁሉን አቀፍ ዘመቻ የከፈቱበት ወቅት ነው፡፡ የተቸገሩ ምእመናንን የዕለት ጉርስ የዓመት ልብስ እንሰጣለን በማለት፣ የቤተክርስቲያኒቱን የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማት እንረዳለን በማለት፣ እንዲሁም ለሆዳቸው ያደሩ ሰዎችን በመጠቀም የቤተክርስቲያን ዋነኛ የፈተና ምንጭ ሆነው ቀጥለዋል፡፡
1.2 አላውያን ነገሥታት
በቤተክርስቲያን ታሪክ ከጌታ ትንሣኤ እስከ 70 ዓ.ም ድረስ ያለው ዘመን ዘመነ ሐዋርያት ከ70 ዓ.ም እስከ 160 ዓ.ም ያለው ደግሞ ዘመነ ሐዋርያነ አበው እንዲሁም ከ16ዐ ዓ.ም እስከ 312 ዓ.ም ያለው ዘመነ ሰማዕታት  በመባል ይታወቃል፡፡
በመጀመሪያዎቹ ሁለት ክፍላተ ዘመናት የነበረው የቤተክርስቲያን አገልግሎት ከአይሁድ ጋር የተደረገ ተጋድሎ ነው፡፡ ይኸውም ምንም እንኳን የአይሁድ ማኅበረሰብ ቃል ኪዳን የተገባለት፣ ትንቢት የተነገረለት፣ በአንድ አምላክ አማኝ ቢሆንም የክርስቶስን አዳኝነትና አምላክነት ላለመቀበል በአመጽ በመግፋቱ፣ እነርሱን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመመለስና ለማቅረብ የተደረገ ጥረት ነበር፡፡
ሦስተኛው ክፍል ግን ቅዱሳን አበው ከአላውያን ነገሥታት ጋር ባደረጉት ተጋድሎ የሚዘከር ዘመነ ሰማዕታት ነው፡፡ በክርስትና ሃይማኖት ትምህርትና በመምህራኑ አማናዊ ምሳሌነት በመላው ሮም የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፍቶ ነበር፡፡ በመሆኑም ለባሮች የነጻነት ትምህርት የተሰበከላቸው ሲሆን ባለጸጋዎችም ቢያምኑ የክርስቶስ አገልጋዮች ለመሆን እንደሚበቁ ተነገራቸው፡፡ /1ቆሮ 7፥22/  የአሕዛብን የቀደመ ትዕቢትና ኩራት የእግዚአብሔር ቃል  ሲያፈራርሰው፤ የአሕዛብን የአመንዝራነት ሕይወት የክርስቲያኖች ቅድሰና አሸነፈው፡፡ በአሕዛብ ልማድ በወንዶች መካከል ሴቶች የክብር ቦታ ያልነበራቸው ሲሆን በክርስትና እኩልነትና መከባበር ታወጀ፡፡
ከዚህ በኋላ ግን ክፉዎች በክርስቲያኖች ላይ የሰውን ሥጋ ይበላሉ፤ ለቄሳር አይታዘዙም፤ ግብር አይከፍሉም፤ የሚሉ ተራና ክፉ ወሬዎችን አወሩ ፡፡ በዚህ የተነሳ እንደነ ዲዮቅልጥያኖስ ያሉ ኢአማኒያን/ከሃድያን/ ነገሥታት ስልጣናቸውን መከታ አድርገው ብዙ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት እንዲያልፉ ያደረጉበት እኩይ ተግባር ፈጸሙ፡፡ ይህም ደጉ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ መንበረ ሥልጣኑን ይዞ ለክርስቲያኖች ሠላም እስኪያወርድላቸው ድረስ የቀጠለ ጉዳይ ነበር፡፡
ቤተክርስቲያን ለምድራዊ ኑሮ ሲባል በተለያየ ሥርዓተ መንግሥት ሥር የሚኖሩ ሰዎችን ነው በሥርዓቷና እና በትውፊቷ እንዲኖሩ የምትጥረው፤ የእርሷ ድርጊት ሁሉ ከአመራራቸው ጋር የማይሄድ የሚመስላቸው ሁሉ እንደየዘመናቸው ሁኔታ መከራን አጽንተውባቸዋል፡፡ ይህም የሁል ጊዜ የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጭ ሆኖ የቀጠለ ጉዳይ ነው፡፡

1.3 የአባቶች አለመግባባት /በአባቶች መካከል አለመግባባት መከሰት/
«የክርስቶስ ፍቅር ገብቷቸው ክርስትናንና ከዚያ የሚከተሉትን ኃላፊነቶችን፣ ክህነትን እስከ ጵጵስና ድረስ «አውቃለሁ፤ እበቃለሁ» ብለው ወይም « ይገባኛል» ብለው ሹመት ፈልገውና ተካሰው ሳይሆን «እኛ አንበቃም ተውን» እያሉ፣ ነገር ግን ለመንጋው የግድ መሪ ስለሚያስፈልገው «እናንተ ለዚህ ሓላፊነት ትበቃላችሁ መንጋውን ጠብቁ» እየተባሉ አደራ ሲጣልባቸው የተሰጣቸውን ከባድ ሓላፊነት የሚጠይቀውን ዋጋ ሁሉ በመክፈል የተወጡ ብዙ ቅዱሳን አባቶች ቤተክርስቲያናችን አሏት፡፡

«በተቃራኒው ደግሞ እነዚህን ሓላፊነቶች ለራሳቸው ግላዊ ክብርና ዝና መጠቀሚያ በማድረግ የክርስቶስን ክብርና በደሙ የዋጃትን ቤተክርስቲያንን ደኅንነትና ዕድገት ሳይሆን የራሳቸውን ምድራዊና ጊዜያዊ ፍላጐት ማስፈጸሚያ መሣሪያ ያደረጉትም ብዙዎች እንደነበሩ የቤተክርስቲያን ታሪክ መስታወት ሆኖ ያሳየናል» /ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱና ትምህርቱ ገጽ 7/
ከዚህ በተጨማሪ አንዳንድ ጊዜ በአሠራርና በአመራር ምክንያት በአባቶች መካከል አለመግባባት ይፈጠራል፡፡ የአባቶች አንድነት የቤተክርስቲያን የአንድነቷ መገለጫ ነው፡፡ ይህ አንድነት በአንድም ይሁን በሌላ ምክንያት ችግር ከገጠመው የቤተክርስቲያን የፈተና ምንጭ ሆኖ መቀጠሉ አይቀርም፤ ይህም በተለይ ለውጭ ጠላቶች በራችንን ወለል አድርጐ የሚከፍትላቸው ነው፡፡
1.4 የምእመናን መንፈሳዊ ሕይወት መዳከም
የክርስትና ሕይወት በየጊዜው በመጠን እየተለካ የሚያድግ ሕንጻ እግዚአብሔር ነው፡፡ ክርስትና በቤተክርስቲያን መሠረተ እምነት /ዶግማ/ በማመን በክርስቶስ ሕግና ሥርዓት መመራትና መኖር ነው፡፡
ምእመናን የቤተክርስቲያንን ድምጽ አልሰማ ብለው ሕይወታቸውን በቃለ እግዚአብሔር ከመምራት ይልቅ በሥጋዊ ፈቃድ ስሜት መመራት ከጀመሩ የቤተክርስቲያን ትልቁ አደጋዋ ነው፡፡ ይህ በሆነ ጊዜ በአባቶችና በምእመናን መካከል መደማመጥ አይኖርም፡፡ በዚህ ወቅት እግዚአብሔር ጸጋውን ይነሳል፤ የምእመናን ማኅበርም በክፉ ይታወካል፡፡
1.5 የግል ጥቅም አጋባሽ የሆኑ ግለሰቦች
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድ ወቅት ይከተሉት ለነበሩት ሰዎች አንድ መሠረታዊ ጥያቄ ጠይቋቸው ነበር፡፡ «ምን ልታዩ መጥታችኋል» /ማቴ 11፥7-1ዐ/ ምንም እንኳን  ጌታ የጠየቀው ስለ ዮሐንስ ቢሆንም እርሱን ስለመከተላቸውም የሚያመለክት ነው፡፡ በመጽሐፍ እንደምናነበው ጌታን ይከተል የነበረው ሕዝብ ሁሉ ትክክለኛና አንድ ዓላማ ብቻ የነበረው አልነበረም፡፡ ይከተሉት የነበሩትን ሰዎች በሦስት ዋና ዋና  ክፍል መመደብ ይቻላል፡፡
ሀ. ሕብስት አበርክቶ ያበላ ስለነበር ጊዜያዊ እንጀራ ለመብላት ለሆዳቸው የሚከተሉት ነበሩ
ለ. የማስተማር ጥበቡን፣ እውቀቱን ለማድነቅ እንዲሁም ዓለምን ሊያድን የመጣ ንጉሥ ምን ዓይነት እነደሚመስል መልኩን ለማየት የሚከተሉት ነበሩ
ሐ. ድውያንን ሲፈውስ ለምጻሞችን ሲያነጻ ሙታንን ሲያነሳ አይተው ከደዌ ሥጋ ብቻ ለመፈወስ የሚከተሉት ነበሩ፡፡
መ.ድውያንን ፈወሰ ለምጻሞችን አነጻ ሙታንን አነሳ እንዲሁም ከተለያዩ ሀጢአትን ከሚሠሩ ጋር ይውላል ያድራል በማለት ለክስ የሚከተሉትም ነበሩ።
እነዚህ ሁሉ ግን የጌታችን የእግር መንገድ ሥራዎች ምድራዊ ሀብት እንጅ ዋነኛ ዓላማዎች አልነበሩም፡፡ የቃሉን ትምህርት ሰምተው ተአምራቱን አይተው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣው ለአድኅኖተ ዓለምና ለእኛ አርዓያ ምሳሌ ሊሆን በመሆኑ ከአምስቱ ገበያ ሕዝብ ግን ይህን ተረድተው የተገኙት መቶ ሃያው ቤተሰብ ብቻ ናቸው፡፡
በቤተክርስቲያን ጉዞ ውስጥ እስከ ዛሬም ድረስ ለሥጋዊ ጥቅማቸው ፤ ወይም አድናቂና አጨብጫቢ ሆነው ብቻ ቤተክርስቲያን ላይ እንደ ክፉ ተባይ የተጣበቁ ግለሰቦች ነበሩ፤ አሉ፡፡ እነዚህ በቤተክርስቲያን አገልግሎት ፍላጐታቸው ሥጋዊ ጥቅማቸው ማጋበስ ብቻ ስለሆነ ከእነርሱ ጋር የማይስማማ አባት፣ ካህን፣ ዲያቆን፣ ምእመን እንዲኖር አይፈልጉም፡፡ ለዚህም ሲሉ የማያሴሩት የክፋት ሴራ ባለመኖሩ ለቤተክርስቲየን አገልግሎት ነቀርሳዎች ሆነዋል፡፡
2.    ፈተናዎች በቤተክርስቲያን ላይ ምን አደረሱ?
በቤተክርስቲያናችን በመናፍቃን፣ በአላውያን ነገስታት፣ በጥቅም አጋባሽ ግለሰቦችና በመሳሰሉት የደረሰባት በደል በዚች አጭር ጽሑፍ ዳስሶ መጨረስ ከንቱ ድካም ይሆናል፡፡ ዋና ዋናዎችን ማንሳት ግን ግድ ነው፡፡
2.1 ቤተክርስቲያንን መከፋፈል፦
በሦስቱ ጉባኤያት /ኒቅያ  ቁስጥንጥንያና ኤፌሶን/ ዶግማዋን አጽንታ፣ ክፉዎችን ለይታ፣ ጥርት ያለውን እምነት ይዛ፣ አንድነቷን ጠብቃ የተጓዘችው አንዲት ዓለም አቀፋዊት ኦርቶዶክሳዊ ቤተክርስቲያን ዛሬ ላለችበት ሁኔታ የበቃችው እነ አርዮስ በጫሩት የምንፍቅን የክህደት እሳት ነው፡፡ዛሬ ክርስቲያን በሚለው መጠሪያ የሚታወቁ ቤተ እምነቶች በዓለም እንዲፈጠሩ የሆነው ከላይ በዘረዘርናቸው ምክንያቶች ነው፡፡
የሕንድ ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያንን የአሳዛኝ ታሪክ ምሳሌ ያደረጋት የመናፍቃን ደባ ነው፡፡ የሮም ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ከኦርቶዶክሳውያኑ ጐራ ተለይታ የኖረችው  እዚህ ግባ በማይባል ፖለቲካዊ / ምድራዊ ሥልጣን/ ምክንያት በተጀመረ ጠብ ነው፡፡
ዛሬ በእኛ ቤተክርስቲያን በአገር ውስጥ አባቶችና በውጭ በሚኖሩት መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ፍጹም ክርስቲያናዊ በሆነ አኳኋን በአጭር ጊዜ ውስጥ ካልተፈታና መፍትሔ ካልተገኘ እንደ ሕንድ ቤተክርስቲያን በእኛም በየአጥቢያው ላለመከፋፈልና ጥቁር ነጥብ ስላለመከሰቱ እርግጠኛ መሆን ይከብዳል፡፡
2.2  ምዕመናን ግራ ማጋባት
ቤተክርስቲያን በአባቶች አለመግባባትና በክህደት ትምህርት በምትፈተንበት ወቅት የሚከሰተው ትልቁ ስጋት /ክስተት/ የምዕመናን ግራ መጋባት ነው፡፡ ይህ ደግሞ እነርሱን ለመቀራመት አሰፍስፈው ለሚጠብቁ የቤተክርስቲያን ጠላቶች የመንጋውን በረት ወለል አድርጐ የሚከፍት ነው፡፡ ዛሬ በአሜሪካ ባለችው ቤተክርስቲያን ከሁለቱም ወገን አይደለንም፤ገለልተኛ ነን፤ግን ጳጳስ እንፈልጋን የሚሉ አብያተ ክርስቲያናትና ምዕመናን የዚህ  ምሳሌዎች ናቸው፡፡
2.3 ጽንፈኝነት፦
በክርስትና የሕይወት ጉዞ ውስጥ እጅግ አደገኛ ከሚባሉ በሽታዎች አንዱና ዋነኛው ጽንፈኝነት ነው፡፡ ያውም ደግሞ ተላላፊ በሽታ ነው፡፡ «በዚህ ዓለም ያሉ ነገሮች አፈጣጠራቸውና ሕይወታቸው ከተለያዩ ነገሮች ረቂቅና ድንቅ በሆነው ጥበብ መለኮታዊ ተመጥኖ የተዘጋጀ ነው፡፡ ይህ መጠን ሲናወጥ ግን ሕይወት አደጋ ላይ ይወድቃል፡፡» /ሐመረ ተዋሕዶ 2000 ዓ.ም ገጽ 12/
«ማዕከላዊ ደረጃ የሌላቸው ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህም እግዚአብሔርና ጣዖታት፤ እውነትና ሐሰት፤ ሕይወትና ሞት ፤መንግሥተ ሰማያትና ገሃነመ እሳት፤ ክርስትናና ከክርስትና ውጭ ያሉ እምነቶችና አስተሳሰቦች.. » /ሐመረ ተዋሕዶ 2000 ዓ.ም ገጽ 13 / እነዚህ በራሳቸው ብቻ ቀዋምያን ከሆኑ ነገሮች ውጪ ያሉትን ግን በመጠን፣ መያዝ መኖር ተገቢ ነው፡፡ «መጠን ማለት» አንተም ተው አንተም ተው» ዓይነት ጉዳይ ሳይሆን ሁሉንም ነገር በራሱ አግባብና በተገቢው መጠን ማድረግና ከዚያ አለማሳለፍ ሲሆን ጽንፈኝነት ደግሞ ከዚህ ከተገቢው ልክና መጠን ማለፍ ነው፡፡» /ሐመረ ተዋሕዶ 2000 ዓ.ም ገጽ 14/
አይሁድን ከክርስትና የለያቸው ክርስቶስ ምድራዊ መንግሥትን አልመሠረተም፤ አንቀበለውም የሚል ጽንፈኛ አስተሳሰብ ነው፡፡ ወደ ክርስትና የመጡትንም ከአሕዛብ ወገን ወደ ክርስትና ከመጡት ጋር ሲያጣላቸው የነበረው « ጥምቀት ያለ ግዝረት ዋጋ የላትም» የሚለው ጽንፈኛ አስተሳሰብ ነው፡፡
ዛሬ ብዙዎችን ከቤተክርስቲያን እየለየ ያለ ይህ የጽንፈኝነት አስተሳሰብ ነው፡፡ ሰባኪ እገሌ እንዲሰብክ ካለተፈቀደለት ጉባኤ አልመጣም፤ ዲያቆን እገሌ እንዲቀድስ ካልሆነ አላስቀድስም፤ እነ እገሌ ወጥተው’ እነ እገሊት ካልተመረጡ ይህንን ማኅበር አልፍልገውም፤ እዚህ  ሰንበት ት/ቤት አልደርስም፤ ብለው የቀሩ ሰዎች በጽንፈኝነት ቀሳፊ ቀስት የተወጉ ናቸው፡፡
ቤተክርስቲያን በተፈተነች ቁጥር አንዱን ጽንፈ ይዘው በማክረርና በመወጠር ከማኅበረ ምእመናን የተለዩትን ቆጥረን አንጨርስም፡፡
ምንተ ንግበር /ምን እናድርግ/?
«ሰውን ብትታገል ብትዋጋ ታሸንፈዋለህ ወይም ያሸንፍሃል ቤተክርስቲያንን ግን ለማሸነፍ አይቻልም ቤተክርስቱያን ሁል ጊዜ ትዋጋለች ተሸንፋ ግን አታውቅም ዲያብሎስ ዝናሩን አራገፈ ቀስቱን ጨረሰ፡፡ ቤተክርስቲያንን ግን አልጎዳትም» ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን በመጥቀስ የጻፉት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የቤተክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ በተሰኘው መጽሐፋቸው ነው / የቤ.ተ. ገጽ 48/። ፈተና የቤተክርስቲያን የመኖሯ መገለጫ እንደሆነ በጽሑፋችን መግቢያ ላይ ገልጸናል፡፡ ነገር ግን ቤተክርስቲያን ፈተና በሚገጥማት ወቅት በሚነሳው ማዕበል ተከፍተን ከመርከቧ ወደ ባሕር እንዳንወርድ ምን ማድረግ ይገባናል? ጥቂት ነጥቦችን እናነሳለን፡፡
3.1 መንፈሳዊ ሕይወትን መጠበቅና ማጽናት ነው
የ አበው አባቶቻችን የተጋድሎ ገድል ስናነብ የምንረዳው ምንም እንኳን ወጥ የሆነ መንፈሳዊ ሕይወት ቢኖራቸውም ከባድ ፈተና በገጠማቸው ጊዜያት ግን የበለጠ ይበረታሉ። በርካታ ቃል ኪዳናትን የተቀበሉት በርካታ መንፈሳዊ መጻሕፍትን የጻፉት የብዙ ጸጋ ባለቤት የሆኑት በፈተና ውስጥ ነው፡፡
የምንማረው ከአባቶቻችን ነውና ቤተክርስቲያን ፈተና ላይ በምትሆን ጊዜ በጋዜጣ በሚጻፈው፣ በድረገጽ በሚለቀቀው «እንዲህ ሆነ እንዲህ ተደረገ» ወሬ ተገፍቶ እርሱን ብቻ በማውራት የራስ ሕይወትን መዘንጋት አይገባም፡፡ የሚሰሙት ዜናዎች፤ የሚፈጸሙት ድርጊቶች የግል መንፈሳዊ ሕይወትን የመሸርሸር አቅማቸው በጣም ከፍተኛ ነው፡፡ ከእኛ የሚጠበቀው የቀደመ መንፈሳዊ ሕይወታችን መጠበቅ ማጽናት እግዚአብሔር አምላክ በፈተና ውስጥ ለቤተክርስቲያን በጐ የሆነውን ሁሉ እንዲያደርግ ጉዳዩን በጸሎት መያዝ መሆን አለበት፡፡
3.2 የቤተክርስቲያንን ድምፅ ብቻ መስማት
ቤተክርስቲያናችን መሠረተ እምነታዊ /ዶግማዊ/ በሆነ ችግር የተፈተነች እንደሆነ የቤተክርስቲያን ቋሚ ምስክር የሆኑ መጻሕፍትን፣ ትውፊተ አበውን፣ የቀድሞ የቤተክርስቲያን ድንጋጌዎችን መጠየቅ፣ ማንበብ በእርሱም ብቻ መመራት ተገቢ ነው፡፡
በአባቶች መካከል አለመግባባት ተፈጥሮ ቤተክርስቲያን በተፈተነች ጊዜ ከግጭቱ ተጠቃሚም ተጐጅም ያልሆኑ በአንድም በሌላም ያልወገኑ አባቶችን ድምፅ ብቻ መስማት ተገቢ ነው፡፡ እንዲሁም ስለ ርዕሰ ጉዳዩ የቀድሞ ሥርዓትና ትውፊት እንዲሁም ትምህርት ምንድን ነው? የሚለውን ማየት ተገቢ ነው፡፡
የትኛውም ወገን’ትውልድ ቢሆን የኃይል ሚዛኑ ስለመዘነለት ብቻ የሚያራግበውን ተቀብሎ በስሜት መነዳት አያስፈልግም፡፡ የቤተክርስቲያን ድምጽ ከቅዱሳት መጻሕፍት ከትውፊትና ከቅዱስ ሲኖዶስ የሚሰማ ነው፡፡ እርሱን ብቻ መስማት ተገቢ ነው፡፡
3.3 ከጽንፍ ራስን መጠበቅ ነው::
በክርስትና ሕይወት የጽንፈኝነትን አደገኛነት ከላይ በጥቂቱ ለመግለጽ ሞክረናል፡፡ የአሁኑ ዘመን ምእመናን የባሕታዊ እገሌ ተከታይ፣ የአቡነ እገሌ ደጋፊ፣ የመምህር እንትና አድናቂ፣ የዘማሪ/ዘማሪት እገሌ ቡድን እየተባባልን መታየታችን የበሽታው ምልክት ነው፡፡ መጨረሻውም መከፋፈል ነው፡፡ አሁን በቅርቡ በተጠናቀቀው የቅዱስ ሲኖደስ ስብሰባ እንኳን ብዙዎቻችን ውሳኔዎችን እንመዝን የነበረው «ማን ምን ተናገረ? የትኛው ጐራ ተሸነፈ? ማን ምን ተደረገ?» በሚሉና በሚመስሉ መስፈርቶች እንጂ ውሳኔው ለቤተክርስቲያን ጠቃሚ ነው ወይስ ሌላ? የሚል አልነበረም፡፡
በእንዲህ አይነቱ ክስተት ማንም አሸናፊ ማንም ተሸናፊ የለም፡፡ ደግ ከተሰራ ቤተክርስቲያን አሸነፈች፤ አበራች፡፡ ሸፍጥ ከተሰራ ቤተክርስቲያን ተጐዳች፤ እውነታው ይሄ ነው፡፡
ከስሜት እንራቅ፤ ከጽንፈኝነት ራሳችንን እንጠብቅ፡፡ ወገንተኝነታችን ለቤተክርስቲያን ብቻ ይሁን፡፡ ያኔ የሰውም የእግዚአብሔርም ፍስሐ ይሆናል ፡፡ አምላከ ቅዱሳን ለዚያ ድል ያብቃን፡፡አሜን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ልሳነ ሰብእ ቀዳማዊ

1. ግእዝ ምስለ ቤተ ክርስቲያን

ቤተ ክርስቲያን ለብዙ ዘመናት የፈተና ገፈታ ቀማሽ በመሆን፣ ልጆቿን እያበረታታች ለሀገራዊ ሀብት መጠበቅም እስከ ሰማዕትነት እያበረከተች በየአድባራቱና ገዳማቱ ጠብቃ አሳድጋ ለዚህ ትውልድና ዘመን ካቆየቻቸው ዕሤቶች አንዱ ግእዝ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ቤተ መዘክር፣ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት ቤት፣ ቤተ ክርስቲያን ግምጃ ቤት፣ ቤተክርስቲያን የሥልጣኔ ማዕከል፣ ቤተ ክርስቲያን ከተማ ሀገር በመሆን ስታገለግል ቆይታለች፡፡

ስለዚህም ነው በሀገሪቱ የታሪክና የመዛግብት ጥናት ላይ የረጅም እድሜ ልምድ ያላቸው ፕሮፌሰር ሪቻድ ፓንክረስት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሀገሪቱ ባህል ጠባቂ ናት ሲሉ በውዳሴ ዘጽድቅ የሚመሰክሩላት፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የግእዝን ሥነ ጽሑፍ ሆነ ቋንቋ እንደሚከተለው ጠብቃ አስረክባናለች፡፡

በየጉባኤያቱ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ማዕከለ ትምህርት በመሆን ለዘመናት ሕዝቡን አገልግላለች፡፡ በራሷ ባሕላዊ ሥርዓተ ትምህርት ዜማውን ቅኔውን ትርጓሜ መጻሕፍቱን በዚሁ ቋንቋ ስታስተላልፍ ቆይታለች፡፡ እነዚህም ትምህርቶች የሚከናወኑበትን ትምህርት ቤት ከቤተክርስቲያኗ ዐውደ ምሕረት ዙሪያ በተዘጋጁ የመቃብር ቤቶች፣ ዙሪያውን  በተሠሩ ጎጆች አልያም በዙሪያዋ በተተከሉ ዐጸዶች አትሮንሷን ዘርግታ፣ አዘጋጅታ፣ ዜማውን አሰምታ፣ ግሱን አስገስሳ ምስጢሩን አብራርታ አስተላልፋለች፡፡ ይህንንም ስታደርግ ለደቀመዛሙርቱ ከሰንበቴው ከደጀ ሰላሙ ረድኤት እያሳተፈች ነው፡፡

በሊቃውንት የሊቃውንት፣ የፍቅር ሀገር፣ ሕይወተ ክርስትና፣ ፍሬ በረከት ስላላቸውና ዘወትር ቃለ እግዚአብሔርን በመናገር፣ ደቀ መዝሙር ሲያጠፋ ሲያርሙ ሲሳሳት ሲያስተካክሉ፣ የተበላሸውን ሲያቀኑ ባሳለፉት ድካም ሀብተ ታሪክን አውርሰዋል፡፡ የደረሷቸውን ቅኔያት፣ የጻፏቸውን መጻሕፍት ዜና መዋዕላቱን ጭምር ሲደጉሱ፣ ሲኮትቱ የተሻለ ቅርጸ ፊደልን ሲያወርሱን ወዘተ ነፍሳቸውን ከሥጋቸው አብልጠው በመኖራቸው ነው፡፡ በመሆኑም ዳዊቱን እየደገሙ፣ መጻሕፍትን እየተረጎሙ ያብራሩበትም በዚሁ ልሳን ነው፡፡ በዚህ ሳይወሰኑ ሌትም ቀንም እንቅልፍ አጥተው ከማኅሌቱ፣ ከሰዓታቱ፣ ከጉባኤ ቤቱ ሳይለዩ ስለ ነገዋ ቤተ ክርስቲያን በመጨነቅ ያስተማሩትን ደቀ መዛሙር «ኦ ወልድየ ጽንዐ በጸጋሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘኅዱር ላዕሌከ በመንፈስ ቅዱስ» ልጄ ሆይ አድሮብህ ባለው በመንፈስ ቅዱስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋው ጽና ምከር አስተምር ብለው የቃል አደራ በመስጠት በየአህጉሩ ሲያሰማሩ ቆይተዋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ጸሎታቸውን ለሀገር በሱባኤ ሲያደርሱ ኖረዋል፡፡

ደቀ መዛሙርቱ ሀገረ ሙላዳቸውን በመተው ደበሎ ለብሰው፣ ቁራሽን ተማምነው፣ አኮፋዳቸውን ከሰሌን አዘጋጅተው፣ ዳዊታቸውን በትከሻቸው አንግበው በትምህርተ ቤተክርስቲያን ዘመናቸውን ያቆዩ ተማሪዎችም ባለውለታ መሆናቸው የማይዘነጋ ነው፡፡ እድሜ ሳይገድባቸው ገና በልጅነት እድሜያቸው ጥሬ እየቆረጠሙ በውርጭ እየተነሡ ሀገር ለሀገር በመዞር ምስጢር ሲሸምቱ የአባቶቻቸውን ትውፊት በቃል በመጽሐፍ ያስተላለፉ ደቀ መዛሙርቱም እነዚሁ ናቸው፡፡ እነዚህም በሌሊት እየተነሡ ከመምህራቸው እግር ሥር ሆነው በብርዱ፣ በቁሩ ሲቀደሱ ሲያስቀድሱ፣ የሌሊቱን ዝናብ ታግሰው ሳይታክቱ በመምህራቸው ጓሮ በትጋት የተማሩባቸውን ጉባኤያት እያስታወሱ ሲያስተላልፉ ኖረዋል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ያለኀፍረት ራሱን ዝቅ አድርጎ በምእመናን ደጃፍ ዐረፍ ብሎ የተገኘውን እየተዘከሩ ወደ ጉባኤው ሲመለሱ እያዜሙ፣ ቅኔውን እየቆጠሩ፣ ወንዙን እየተሻገሩ፣ ተራራውን እየወጡ፣ እየወረዱ የአራዊቱን ድምጽ እየሰሙ፣ ተፈጥሮን እየቃኙ፣ ምስጢርን እያዩ ያዩትንም በቅኔው እየቀመሙ ለነባር ሲያስተላልፉ ቆይተዋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ለክብረ በዓሉ ያለውን ቀለም በአፋፍ ላይ ሆነው እየቀጸሉ በጎጆአቸው ሌሊቱን ሲያዜሙ በራሳቸው ቋንቋ «አዛኘን» እስኪ በልልኝ  በመባባል እየተሳሳሉ ለዘመናት ትምህርቱን አስተላልፈዋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን መምህራቸውን በእርሻ፣ በማሳ፣ በሥራ እየረዱ ነው፡፡

 
ምዕመናን ለሃይማኖታቸውና ለሀገራቸው ባላቸው ፍቅር ሃይማኖታቸውን ከቤተ ክርስቲያን አጣምረው ኖረዋል፡፡ በባህል ግንባታውም ተሳትፈዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ተረካቢ ተማሪንም ከመሶባቸው ማዕድ ሳይሰስቱ እየመገቡ ሲያስተምሩ ቆይተዋል፡፡ ቤተክርስቲያን እንድትገለገል ጧፉን መጋረጃውን አሥራቱን ሲያስገቡ ባደረጉት አስተዋፅኦ የቤተ ክርስቲያኗ ሀብቷ እንዲህ ሊተላለፍ ችሏል፡፡ ዋዜማ እየደገሱ ቁመት ሲያስቆሙ ዕድሞ ሲያስከብሩ ኖረዋል፡፡

2. የግእዝ ቋንቋ እንዲያድግ ለምን አስፈለገ?

ባህል በቋንቋ ይለካል፡፡ እምነቶች ሥነ ሕዝብ ማኅበራዊ መሠረቶች /ዐምዶች ልምዶች ዕውቀቶች ሁሉ በቋንቋ አሉ፡፡ በአደጋ ላይ ያለ ቋንቋ ማለትም በአደጋ ላይ ያለ ዕውቀት አሳሳቢ፤ ባህል ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ስለ አገባብ የሚታወቀው ዕውቀት ካፀፀ መሠረት የለሽ ድካምን ያስከትላል፡፡

በመሆኑም ቋንቋ የኅብረተሰብእ /የአንድ ሕዝብ አካል ነው፡፡ ስለ ሕይወት ባህል ልምድ የሚፈስ ዕውቀት ሁሉ ትርጉም የሚኖረው በራስ ቋንቋ በሚገኝ ዕውቀት እንጂ የተጻፈን በመቀበል አለመሆኑ ደግሞ የራስ ቋንቋን ማወቅ ወሳኝ መሆኑን ያሳያል፡፡ ልሳናት በአባቶች ቅድመ አያቶች ቀሩ ማለት የልጆች ሀገራዊ አንደበታቸው ማንነት የሚጠብቁበት ኃይል ጠፋ ማለት ነው፡፡ የእኛ ማንነትና ታሪካችን ያለው የተቆራኘው በብዙ መንገድ ከቋንቋችን /ከግእዝ ጋር ነውና ያለበትን ደረጃ ልንመረምርና ልናስተውለው ይገባል፡፡ ሌላው ይቅርና መለያችን ልዩነታችን እንኳን በቋንቋችን ሰዋስው አገባብ ሊታወቅ ይችላል፡፡ ቋንቋችን ካልተጠበቀ የሚተላለፈው ዕውቀት ትውፊት ባለበት ይቆማል፡፡ አብሮ አስሮ የያዘቸውን እውቀቶች ፍልስፍናዎች ሁሉ ይዞ ይጠፋል፡፡ ነገር ሁሉ በአዲስ ይጀምራል፡፡ ሥር የሌለው በአሸዋ የተገነባ ሕንፃን ይመስላል፡፡ የሌሎች የባህል ጎርፍ በመጣ ጊዜ በቀላሉ ይወድቃል፡፡ ቋንቋን መጠበቅ ብቻ ሳይሆን እንደገና ልንጠቀምበት ይገባል፡፡ በስደት፣ በዝርፊያ በዓለም ዙሪያ በየቦታው ያሉትን የሥነ ጽሑፍ ሀብቶች ሊመረምሩ የሚችሉ ልጆች ሊተኩ ያስፈልጋል፡፡ የተበረዘውን ማቅናትና የጠፋውን ታሪክ መፈለግ፣ የተለየንን የጥበብ ምንጭ ፍለጋ መውጣት መውረድ ያስፈልጋል፡፡ ሊጠፉ የተቃረቡትንም መጠበቅና ብሎም ዘመኑ ባፈራቸው መሳሪያዎች ተጠቅሞ በመቅረጽ ለትውልዱ ማስተላለፍ ትልቁ ኃላፊነት ይኸው ነው፡፡

አፍሪካውያን ዛሬ ቋንቋቸውን ለመጠበቅ የሚያደክማቸው ለብዙ ዘመናት በተሰላ እቅድ ሥር ተጽዕኖ በመውደቃቸውና በሌላኛው የቅኝ ግዛት መንገድ ማለፋቸው ነው። እንዳልነው ይህ ችግር ደግሞ ዛሬም ከአፍሪካ ምድር ስላልተወገደ በአደጋ ላይ የነበሩ ዕውቀቶች ሁሉ ጠፍተዋል፡፡ መፍቀርያነ ባህል አፍረንጅም በመብዛታቸው ነባሩ/ የአከባቢው መንፈሳዊውም ሆነ ቁስ አካላዊው ዕውቀት እየተረሳ መጥቷል፡፡ ይህንን እየተረሳ ያለ ሀብት ደግሞ ለመጠበቅ ልምዱ ያላቸው ወላጆችና ሽማግሌዎች አስረካቢ ሕፃናት ተረካቢ ሊሆኑለት ይገባል፡፡ እንግሊዘኛቸውን ሲናገሩ በማበላሸታቸው የሚስቁ ይቅርታ የሚጠይቁትን ወጣቶችን ልብ አማርኛን ግእዝን ግን በማበላሸታቸው ግን ይቅርታ የማይጠይቁትን አእምሮ ሊያጠቁት ይችላሉ፡፡ በዚያውም ላይ የውጪውን ቋንቋ በመጠቀም የአንደበታቸው አርአያነት ብቻ ሳይሆን መልዕክቱ የተዛባ እየሆነ መጥቷል፡፡

 

በዓለም እያሉ ከዓለም ውጪ መኖር

በዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በበሳል ትምህርቱ በመንፈሳዊ ጥብዐቱና በፍጹም መንፈሳዊ ሕይወቱ በቤተ ክርስቲያናችን የታወቀ አባት ሲሆን ኑሮውም የብህትውና ነበር። ካስተማራቸው በርካታ ትምህርቶቹ መካከል ውስጥ አንድ ክርስቲያን በምድር ሲኖር ሰማያዊውን ሕይወት እንዲኖር ነው። ይህንንም ያስተማረበትን ትምህርት እንዲህ አቅርበነዋል፡፡

“እግዚአብሔር የሚወዳችሁ እግዚአብሔርን የምትወዱ ወንድሞቼ ሆይ እነሆ ሰማያውያን ሆነናል፡፡ ዘበሰማያት የሚያሰኝ ሥጋውንና ደሙን ተቀብለናል፡፡ እንዲህ ከሆነ ከዚህ ነገር የተነሣ እንፈራ ዘንድ እንንቀጠቀጥ ዘንድ ይገባናል፡፡ ሕሊናችንም ሰማያዊውን ማሰብ ትቶ ምድራዊውን ማሰብ እንዳይሆን መሆን ይገባናል፡፡ ሰማያዊነትን የሚወድ ሰው ምድራዊውን እንዳያስብ መሆን ይገባዋልና፡፡ ምድራዊውን ነገር ማሰብ ሰማያዊውን ነገር አለማሰብ ከክፉ ሕሊና ከክፉ ፈቃድ የሚገኝ ስለሆነ፡፡ በዚህ ዓለም እየኖርን እንደሌለን መሆን ይገባናል፡፡ ሰማያዊ አነዋወርን የሚወድ ሰው በዚህ ዓለም እየኖረ እንደሌለ መሆን ይገባዋልና፡፡ በዚህ እየኖሩ እንደሌሉ መሆን ለበጎ ሕሊና ከበጎ ፈቃድ የሚገኝ ስለሆነ፡፡”

ለአምላካችን ክብር ምስጋና ይግባውና እኛ በምድር ሳለን በባለሟልነት ወደ እግዚአብሔር ከቀረብን በምድር ሳለን ፍጹማን ሆነን ሰማያውያን እንድንሆን ዛሬ ምን ያተጋናል? “የሰማይን ጌታ ካየሁት እኔ ሰማያዊ እሆናለሁና፡፡ እርሱ ጌታ አባቴና እኔ መጥተን እናድርበታለን” እንዳለ፡፡ ወንድሞች ሆይ እንዲህም ከሆነ  ራሳችንን ማኅደረ እግዚአብሔር እናደርግ ዘንድ ይገባናል፡፡
ሰማይ እጅግ ያማረች ናትና፤ በተፈጥሮዋም ፈጽማ የበራች ናትና በክረምት አትጠቁርምና መልካም አይለወጥምና ራሳችንን በሰማይ እናድርግ፡፡ ደመናትም መጥተው ከታች ቢሸፍኑዋት ከላይ የሚያበራ ብርሃን አላት፡፡ እንደዚሁ እኛም ጨለማ የማያፈራርቀው እውነተኛ ፀሐይ ጌታችንን ገንዘብ እናድርግ፡፡
አስቀድሞ እስካሁን በሰማይ እንሆን ዘንድ ይቻለናል ብዬ ተናገርሁ፡፡ ዳግመኛም ከእንግዲህ ወዲህ ከሰማይ ይልቅ ያማርን የተወደድን እንሆን ዘንድ ይቻለናል ብዬ እናገራለሁ፡፡ ፀሐይን የፈጠረ ጌታ ክብር ምስጋና ይግባውና  በውስጥ በአፍአ ቢያድረብን በእውነት ከሰማይ ይልቅ ያማርን የተወደድን እንሆናለን ብዬ እመልሳለሁ፡፡
ሰማይስ ንጽሕት ናት ብርይት ናት፡፡ በክረምት ደመና በሌሊት ጨለማ አያገኛትም፡፡ እንደዚህም ከሆነ መከራ የሚያመጣብንን፤ ቀቢጸ ተስፋ፤  ከሚያመጣብን ጠላት ተንኮል እንታገሥ ዘንድ ይገባናል፡፡
ከምድራዊ ሥራ የራቅን የተለየን እንሆን ዘንድ ይገባናል?ሰማይ ከምድር የራቀች ናት፡፡ እንደዚህም ሁሉ ሰውነታችንን ምድራዊ ነገር ከማሰብ አርቀን ሰማያዊ ነገር እናስብ ዘንድ ይገባናል፡፡ ማኅደረ እግዚአብሔር እንሁን፡፡ ትሩፋት ሠርተን ከፍጹምነት እንድረስ፡፡
ከዚህ በኋላ  እንደ ጉንዳን እንደ ትል እናያቸዋለን፡፡ይህ ዓለምና በዓለም ያለው ሃብት ሁሉ አላፊ ጠፊ እንደሆነ እንረዳለን እናያለን። ድኃውን ባለጸጋውን ብቻ አይደለም፡፡ ንጉሡንም ራስ ቢትወደዱንም ቢሆን እንዲህ አድርገን እስከማየት ድረስ ነው እንጂ፡፡ የንቀተ ያይደለ የብቃት ነውና እንዲህ አለ፡፡ ያን ጊዜ ንጉሡን ይጐዳናል አንድም ይጠቅመናል ብለን አናየውምና፡፡ ሕዝባዊውን አይጐዳንም አይጠቅመንም ብለን ለይተን አናውቅምና፡፡ ወርቁንም ብሩንም ለይተን አንድም ይጠቅመናል ብለን አናውቅምና፡፡ ከቀይ ሐር ከነጭ ሐር የተሠራውንም ልብስ ለይተን አንድም ይጠቅመናል ብለን አናውቀውምና እንደትል እናያቸዋለን፡፡
በዚያን ጊዜ ሁከት ሥጋዊ ፍርሃት ሥጋዊ የለም፡፡ በዚህ ዓለም ለሚኖር ሰው ከዚህን ያህል ማዕረግ መድረስ እንደምን ይቻለዋል የሚል ሰው ቢኖር ከዚህ ማዕረግ የደረሱ አበውን ጠቅሰን እንመልስለታለን፡፡ ንኡድ ክቡር ጳውሎስ በዚህ ዓለም ይኖር አልነበረምን፡፡ በዚህ ዓለም ሳለ ከሰማይ ደርሶ ከዚያ ተመልሶ የሰማይን አነዋወር በውኑ ይናገራል ብዬ እመልስለታለሁ፡፡ እርሱ ከሰማይ መድረሱን ለምን እናገራለሁ እግዚአብሔርን እናገኘው ዘንድ ካሰብን ፍቅሩን ክብሩን እንደሚገልጽልን እንረዳለን፡፡
እንዲህ ከሆነ የማይታየውን እንጂ የሚታየውን ዓለም አንመልከት፡፡ ጳውሎስ የሚታየውን ዓለም ይመለከት እንዳልነበረ ተረዳኽን? ወዳጄ ሆይ ከምድራዊ ግብር ሕሊናውን በለየ ጊዜ ከሁሉ በላይ እንዳደረገው ተረዳህን? ከጠፈር ብቻ ከዓለም መላእክት ብቻ አይደለም፡፡ የሉም እንጂ ያሉ ቢሆን ከሌላውም ፍጥረት በላይ እንዲያደርገው ተረዳህን?
መንግሥተ ሰማያት መግባትን ተስፋ አድርገን ግን ከትሩፋት ብንለይ በንዋመ ሀኬት /ከክፋትና ከተንኮል እንቅልፍ/ ብንያዝ ፈጽሞ ትሩፋት መሥራት አይቻለንም፡፡ መንግሥተ ሰማያትንም መውረስ አይቻለንም፡፡ እንዲህም ከሆነ ፈጽሞ ትሩፋት መሥራትን ትወዱ ዘንድ መንግሥተ ሰማያትን ትወዱ ዘንድ ወንድሞቼ ሆይ እማልዳችኋለሁ፡፡
የቅዱሱ በረከት ከሁላችን ጋር  ፀንቶ ይኑር።

/ምንጭ፡- ተግሣፅ ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወረቅ ገጽ 175-184/