የማይሞተው ሞተ!
በመዝሙርና ሥነ ጥበባት ክፍል
ጥቅምት ፳፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
ልዑል ሆይ ክንድህን ስደድ
ናማ ውረድ
ና ተወለድ
ብለው ነቢያት በጾም ጸሎት ተጉ ጮኹ!
ጨለማውን አስወግዶ ብርሃኑን ያበራልን
አንጠፋ ዘንድ በፍጹም ፍቅር የራራልን
በግብዞች በአይሁድ ሥርዓት
በሕጋቸው እንደጻፉት
የሾህ አክሊል ተቀዳጅቶ
መጻጻውን ተጎንጭቶ
…..
እርሱ ሞተ ሊሰጥ ሕይወት
ወየው በሉ አልቅሱለት፤
የእጁን መዳን ያገኛችሁ የጌንሴሬጥ ድውይ ሁሉ
ለኢየሱስ አልቅሱለት፤ ፍዳን ስላያት በመስቀሉ
የ፲፪ ዘመን ሥቃይ በልብሱ ጫፍ ………
በቅጽበት ውስጥ የጠፋልሽ
ተገረፈ፤ ተንገላታ፤ የማይሞተው ሞትን ሞተ፤ ……..
ያ ርኅሩኅ ቸር መዳኒትሽ
ኢያሮስ የት ነው ያለህ!
ያ’ዓለም ጌታ ተተፋበት ሴት ልጅህን ያዳነልህ!
እመቤቴ የልጅሽን መከራውን እንዴት ቻልሽው አልልሽም
ቅዱስ ዳዊት በእሳት ፈረስ ሰባቱ ኃያል …..
መላእክቱ ካንቺ መጥተው ቢያፅናኑሽም
ለሦስት ቀን የአንዱ ልጅሽ ከሞቱ ይልቅ አሟሟቱ ….
እያስነባሽ እህል ውኃ እንኳን አልቀመስሽም
አብ ሆይ ማረን!
መንፈስ ቅዱስ ተዘከረን!
በልጅህ ደም የተገዛን ለመሆኑ አላወቅንም ዋጋችንን
ጽድቃችንም የመርገም ጨርቅ ከንቱ ሆኖ
መኖሪያችን በሲኦል ቋት ተወስኖ
ለዘመናት ስንገረፍ በእሳት ላንቃ
ያበቃ ዘንድ ይህ እንግልት ይህ ሰቆቃ
እሰይ እሰይ ይኸው አሁን የምሥራች
የሞት ዐዋጅ ተሻረልን፤ ገነት ዳግም ተከፈተች
የጥሉ ግድግዳ ፍርሶ ሰላም ሆኗል ከላይም ከታች
፶፻፭፻ የንስሐ የጣር ዘመን ተፈፀመ
በደላችን ተሰርዞ በክርስቶስ ደም ታተመ::
