menekosate 4 2

ከታላላቅ ገዳማት ለመጡ አባቶች አቀባበል ተደረገ

ታኅሣሥ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

menekosate 4 2

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን ታላላቅ ገዳማት ለመጡ አበምኔቶችና እመምኔቶች አቀባበል ተደረገ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ለማሳካት የገዳማት ድርሻ በሚል በተዘጋጀው ዐውደ ጥናትና ለአምስት ቀናት በሚቆየው ሥልጠና፤ እንዲሁም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  ላይ ታላቅ አሻራቸውን ትተው ያለፉትን የታላቁ አባት አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የገድል መጽሐፍ ምረቃ ላይ ለመገኘት ከሃምሳ በላይ ለሚደርሱ ገዳማት አበምኔቶችና እመምኔቶች በተደረገው ጥሪ መሠረት ከማክሰኞ ጀምሮ ርቀቱ ሳይገድባቸው አዲስ አበባ በመግባት ላይ ሰንብተዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም  ዝግጅቱን አጠናቆ በጉጉት ከመጠባበቅ አልፎ በአክብሮት እየተቀበላቸው ይገኛል፡፡

 

ዓርብ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አገልጋዮች በማኅበሩ ሕንፃ 6ኛ ፎቅ ላይ ለአባቶች ማረፊያ ቦታ ለማዘጋጀት በመሯሯጥ ላይ ነው የዋሉት፡፡ ፍራሽ፤ አንሶላ፤ ምንጣፍ፤ ብርድ ልብስ አሰገብተው እያነጠፉ አባቶችን እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት በመቀበል ላይ ናቸው፡፡

 

ማኅበሩ ይህንን ሓላፊነት ለመወጣት አባቶችን በመቀበልና በማስተናገድ አሰተዋጽኦ እንዲያደርጉ ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ለሚገኙ መንፈሳዊ ማኅበራትና በጎ አድራጊ ምእመናን ጥሪ አድርጓል፡፡ በዚህም መሠረት ለአገልግሎቱ ከጧት ጀምሮ የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር አባላት ለአባቶች የሚሆነውን ምግብ በማዘጋጀት ላይ ተጠምደዋል፡፡  አመሻሽ ላይ የማኅበሩ ዋናው ማእከል ግቢ ከ55 በላይ በሚደርሱ ገዳማት በመጡ አበምኔቶችና እመምኔቶች ደምቋል፡፡ ሁሉም የታቀደውን በጎ ዓላማ ለማሳካት በመንቀሳቀስ ላይ ነው፡፡ አባቶች ልጆቻቸውን ለመባረክ ደከመኝ ሰለቸን አላሉም፡፡ ልጆችም በረከት ለመቀበል አባቶች እግር ሥር ከመውደቅ አልሰነፉም፡፡ ፍጹም ክርስቲያናዊ መገለጫ የሆነውን ትሕትና በአባቶችም ሆነ በልጆች ዘንድ ይነበባል፡፡ በአባቶችና በመንፈስ ልጆቻቸው መካከል የሚታየው ቁርኝት ላስተዋለው ያስገርማል፡፡ በአካል ብቻ ሳይሆን በመንፈስም ክርስትና ያስተሳሰረው አንድነት፡፡

 

ምሽት 12 ሰዓት ሲሆን ደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር አባላት 6ኛው ፎቅ ኮሪደር መግቢያ ላይ ውሃ በባልዲና በጀሪካን ሞልተው ለበረከት ያለ እያገዛቸው 6ቱን ፎቅ ይወጣሉ ይወርዳሉ፡፡ የአባቶችን እግር ለማጠብ ሁሉም በመሽቀዳደም ላይ ቢሆንም ሁሉም ከበረከቱ ይሳተፍ ዘንድ በየተራ ለማጠብ አንድ ሰው የአንደ አባት እግር እንዲያጥብ መመሪያ ተሠጠ፡፡ ሰባት የሚደርሱ ሳፋዎች ከነውሃቸው ተቀምጠው አባቶችን ይጠባበቃሉ፡፡ አባላቱ የአባቶችን እግር ለማጠብ ተሰልፈዋል፡፡ አባቶች ከማረፊያቸው እየወጡ ልጆቻቸውን እየባረኩ በትሕትናና ፍቅር በታጀበ መስተንግዶ በልጆቻቸው እግራቸውን ታጠቡ፡፡

 

በቀጣይነት የተካሄደው ለአባቶች ማእድ ማቅረብ ሲሆን የዕለቱን ሙሉ ወጪውንና መስተንግዶውን የቻለው ደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር ነው፡፡ አባላቱም ለአባቶች ያዘጋጁትን ማእድ በማቅረብ ሳይሰቀቁ እንዲመገቡ በመጋበዝ ምን ይጨመር? እያሉ ይጠይቃሉ፤ ወጥ ያወጣሉ እንጀራ ይጨምራሉ፡፡ አባቶች ትሕትናን እንደተላበሱ ለኛ ይህ አይገባም የሚሉ ይመስላሉ፡፡ ደስታ ግን ይነበብባቸዋል፡፡

 

menekosate 2 2ማእዱን እንደተመገቡ  የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት ለማስተላለፍ ቅድሚያውን ወሰዱ፡፡ “የቤተ ክርስቲያን መሠረቷ ገዳማት ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጠነከረች የሚባለውም የገዳማት ጥንካሬ የሚያመጣው ነውና በዚህ ሁኔታ ላይ እንድንወያይ፤ ነገ ምን ማድረግ እንደሚገባን እንድንነጋገር፤ እኛም የምናስበውን ለማሳየት እንድንችል እንድትመክሩን፤ እንድተጸልዩልን ነው የተሰባሰብነው፡፡ እናንተን ለማየት በመታደላችን እጅግ ደስተኞች ነን፡፡ ቀሪውን ጊዜም መልካም ነገር የምናቅድበትና የምንፈጽምበት እንዲሆን እንመኛለን” ያሉ ሲሆን ደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር ላከናወነው አርአያነት ያለው ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

 

የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳዊ የአገልግሎት ማኅበር ተወካይ አቶ ሙሉጌታ በመርሐ ግብሩ ላይ የተሰማቸውን እንዲገልጹ እድሉ የተሰጣቸው ሲሆን “እግዚአብሔር ዛሬ ታላቅ ነገር አድርጎልናል፡፡ በረከት ለማግኘት ከከተማ ወደ ገጠር ነበር የምንወጣው፡፡ እግዚአብሔር የማይታሰብ ነገር አደረገልን፡፡ ሰው እንጨት ሊቆርጥ ወደ ተራራ ይወጣል እንጂ ተራራው ከነ እንጨቱ ወደ ሰው አይመጣም፡፡ እግዚአብሔር የሚሳነው ነገር ስለሌለ ዛሬ አባቶቻችንን ከነበረከታቸው ወደ እኛ አመጣቸው፡፡ አባቶቻችን እናንተ ባትኖሩ እኛም አንኖርም፡፡ እግዚአብሔር እናንተን ስለሰጠን ደስተኞች ነን” ብለዋል፡፡

 

በመጨረሻም አባቶች ከገዳም ወጥተው አዲስ አካባቢ ላይ የሚገኙ  በመሆናቸው ምግቡም ሆነ ውኃው በመለወጡ ምክንያት ሥጋዊ ሕመምmenekosate 2 1 ቢሰማቸው የማኅበሩ አባላት የሆኑ የሕክምና ዶክተሮችና ነርሶች 24 ሰዓት እነሱን ለማገልገል መመደባቸው ተገለጸላቸው፡፡ እንዲሁም ማንኛውንም አገልግሎት ቢፈልጉ እነሱን ለማገልገል የተመደቡ ወንድሞችና እኅቶች ስለሚገኙ የሚሹትን ነገር ሳይሰቀቁ እንዲጠይቁ በማሳሰብ የምሽቱ መርሐ ግብር በአባቶች ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

 

ይቆየን……….