በበረት ውስጥ እነሆ ተወለደ!
በመዝሙርና ሥነ ጥበባት ክፍል
ታኅሣሥ ፳፰፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት
ያቺ ድንግል ቤተ መቅደስ ሆና ሐርና ወርቅ ስታስማማ፣
መልአኩ የምትወልጅው ኢየሱስ ነው ያላትን ቃል ሳታቅማማ፣
የሚፈውስ ድውያንን፣
የሚያበራ ዕውራንን ፣
የሚተረትር ሽባዎችን ፣
የሚያነጻ ለምጻሞችን ፣
የሚያወጣ አጋንንትን፣
ከስም በላይ ስም የሆነ፣
አልፋ ኦሜጋ የታመነ፣
ድንቅ መካር ሰው መሆንን የወደደ፣
በበረት ውስጥ እነሆ አሁን ተወለደ!
በአርያም የሚኖሩት መላእክቱ፣ ተመልክተው አምላክ ሲያዝን ለፍጥረቱ፣
ግርግም ከበው የዚያ ሕፃን ሠራዊቱ፣
በሰማያት አመስግነው እግዚአብሔርን
በምድር ላይ ለሰውም ልጅ ሰላም ይሁን
ብለው ዘምረው፣ ቤተ ልሔም የምድር ዙፋን፣
በአርያም ተሸክመው ቅዱስ አንተ የሚሉትን፣
ድንግል ማርያም ወዮሴፍ ላም አህያ ተመስለው አርባዕቱን፣
እነርሱ አንቺን ተሸክመው አንቺ ድገሞ ጸባኦትን
የአስተርእዮ ዘመን ሆኖ በምድር ላይ ሲከናወን
የሰማዩ ድንቅ ሥራ፣ ከበረት ውስጥ ሲፈነጥቅ ድህነት ፈውስን
ያነገበ የጽድቅ ጮራን፣
አንቺ ቅድስት ቤተ ልሔም፣
ቅጠል ለብሶ እንደ ሕፃን እያነባ መድኃኔ ዓለም፣
ኃያል ንጉሥ እርቃን ሆኖ ባንቺ ሲድር አልፈራሽም
እንደ ባሕር አልሸሸሽም
እንደ እምቦሳም አልዘለልሽም፡፡
እነ ኪሩብ በነደ እሳት የተሠሩ፣
በሁለት ክንፍ በዓለም ዙሪያ የሚበሩ፣
በመለኮት እሳትነት እንዳይጠፉ በሁለት ክንፍ ፊታቸውን የሠወሩ፣
በቀራቸው በሁለቱ እግራቸውን የጠፈሩ፣
- ቅዱስ (፫) ብለው ያለፋታ በመንቀጥቀጥ የሚያመልኩት፣
በግርግም ውስጥ እንደ ሕፃን ሲያለቅስ አይተው ምንስ አሉት
ፀሐይና ከዋክብትን ለፈጠረ፣
በልዩ ጌጥ ዓለማትን ላሳመረ፣
ነገሥተ ተርሴስ ወደሴያት፣
እጅ መንሻ አመሃውን ላመጡለት፣
ከዋክብትን በስማቸው ለሚጠራ፣
ፍጥረታትን ያለሳንካ ለሚሠራ፣
ከክብር አንሶ በራፊ ጨርቅ ተጠቅልሎ፣
አምላክ ሳለ ፍጡር መስሎ እንደ ነዳይ ተጎሳቁሎ፣
የዚያ ሌሊት ቢያይል ቁሩ፣
በደመ ነፍስ የሚኖሩ ትንፋሽ ሰጥተው ሲገብሩ፣
መላእክቱ ቅዱስ(፫) ብለው በፍቅር ሆነው
የሚያመልኩት፣ በግርግም ውስጥ እንደ ሕፃን ሲያለቅስ አይተው
ምንስ አሉት ጽድቃችንም የመርገም ጨርቅ ከንቱ ሆኖ፣
መኖሪያችን በሲኦል ቋት ተወስኖ፣
ለዘመናት ስንገረፍ በእሳት ላንቃ፣
ያበቃ ዘንድ ይህ እንግልት ይህ ሰቆቃ፣
ልዑል ሁይ ክንድህን ስደድ፣
ናማ ውረድ
ና ተወለድ
ብለው ጻድቃን ሲጸልዩ ለዘመናት ፣
እርግማኑን ይሽረው ዘንድ በምርቃት፣
እነሆ አሁን
ጨለማውን አስወግዶ ብርሃኑን ያበራልን፣
ከጎሞራ ያልመሰለን ከሶዶም ግብር ያልደመረን፣
ሰማያትን በደመና የሚጋርድ፣
ተወለደ በዐውድ
እሰይ እሰይ ይኸው አሁን የምሥራች፣
የጸብ ግርዶሽ ተቀዳዶ ሰላም ሆኗል በላ በታች፡፡
፶፻፭፻ የንስሐ የጣር ዘመን ተፈጸመ
አምላክ ወሰብእ በግርግም ውስጥ ከበጎች ጋር ከተመ!
