የቅርሶች ዘረፋን ለመከላከል

የኢትየጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የረጅም ዘመን ታሪክና የበርካታ ውድና ምትክ የሌላቸው እንዲሁም ማንኛውም መጠን ያለው ገንዘብ የማይተካቸው ታሪካዊና ዓለማቀፋዊ እውቅና ያላቸው ቅርሶች ባለቤት ነች፡፡ እነዚህ ሃይማኖታዊ እና ተፈጥሮአዊ ቅርሶቻችን ከቀደምት አባቶቻችንና አያቶቻችን የወረሰናቸው እኛም በተራችን ጠብቀንና ተንከባክበን ለቤተክርስቲያን ዕድገትና ለሀገራዊ ልማት እያዋልን ለመጪው ትውልድ የምናስተላልፋቸው መተኪያ የሌላቸው እሴቶቻችን ናቸው፡፡ ቅርሶች ያለፈውን፣ ነባሩንና ተተኪውን ትውልድ የሚያገናኙ የኅብረ ትውልድ ድልድዮች ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የእነዚህ ንዋይ ሊተምነው የማይችል ቅርሶች ግምጃ ቤት መሆኗ እና እኛም ልጆቿ የዚህ ታሪክ ተረካቢዎች በመሆናቸን መንፈሳዊ ፍስሐ ይሰማናል፡፡

ስለ አገራችን ቅርስ ሲነሣ በአብዛኛው በቅርስነት የተመዘገቡትና የሚጎበኙት የቤተክርስቲያናችን ቅርሶች ናቸው፡፡ ይህም ሁኔታ የኢትዮጵያ ታሪክና የቤተክርስቲያን ታሪክ የማይነጣጠሉ የአንድ ሣንቲም ሁለት ገጽታዎች አድርጓቸዋል፡፡ ስለዚህ ሁላችንም የሀገሪቱ ዜጎች ስለ ቅርስ ጥበቃ የሚኖረን ግንዛቤ ለታሪካችን ካለን አመለካከት የሚነሳ ነው፡፡ አንድ ሕዝብ ቅርስ አለው ስንል ታሪክ አለው፣ ክብር አለው፣ ተደማጭነት እንዲያገኝ የሚያደርግ ማሰረጃ አለው ማለት ስለሆነ ለቅርስ የሚደረግ እንክብካቤና ጥበቃ በታሪክ መዘክርነት ለሚቀርብ ማስረጃ የሚደረግ ጥበቃ መሆኑን ተገንዝበን ለቅርስ ጥበቃው ከግል ፍላጎትና እምነት ነፃ ሆነን ሀገራዊና ሕዝባዊ አስተያየትን ማዳበር ያስፈልጋል፡፡
 
ይሁን እንጂ ዛሬ ብዙ ሃይማኖታዊ ተፈጥሯዊና ታሪካዊ የቅርስ ሀብት እንዳለን ስንገልጽ፣ በርካታ ቅርሶቻችንን በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች ምክንያት ማጣታችን መዘንጋት የለብንም፡፡ እንዲሁም እያየን ነው፡፡ ይልቁንም አሁን በእጃችን ካለው የቅርስ ሀብታችን አብዛኛዎቹ አንድም ባሳለፍናቸው የእርስ በእርስ ግጭቶችና ያለተቋረጡ የባዕድ ወራሪዎችን ለመከላከል በተደረጉ ጦርነቶች ወድመዋል ተመዝብረዋል፡፡ ከዚያም ያለፈው በራሳችን ሰዎች፣ በወራሪ ኃይሎች፣ በጎብኚዎች፣ በተመራማሪነት ስምና በልዩ ልዩ ዲኘሎማሲያዊ መብቶች ሽፋን በየጊዜው በሚመጡ ግለሰቦች ተዘርፈው ተወስደዋል፡፡
 
በጦርነት የወደመውን የቅርስ ሀብታችንን «የፈሰሰ ውሃ» እንዲሉ አበው መፍትሔ ባናገኝለትም እንኳ እጅግ ድንቅ የሆኑ ታሪካዊና ሃይማኖታዊ እንዲሁም ባሕላዊ ቅርሶቻችን ታሪኩ ታሪካቸው ባሕሉ ባሕላቸው፤ ሆኖ በማይዘክሩለት ባዕዳን ሀገራት እጅ ተከማችተው ይገኛሉ፡፡ ለእነዚህ አካላት የገቢ ምንጭ ሆነዋል እነዚህን ቅርሶች ስለ ሀገሩ ባሕል፣ ታሪክና ሃይማኖት እንዲሁም ወግ ለማጥናት የፈለገ ኢትዮጵያዊ ተመራማሪ ከፍተኛ ገንዘብ  በማውጣት ያባቶቹን ሀብትና የእሱነቱን መገለጫ የታሪክ ቅርስ መረጃዎችን ለማግኘት በባዕዳን ሙዚየሞችና ቤተ መጻሕፍት እየዞረ የመንከራተቱ መራር እውነት በብዙ ወንድሞቻችን አንደበት በየጊዜው የሚነገር ነው፡፡ ይሄን እውነት እነርሱ እንኳን ብንለው ችግሩ ከቶ ሊያስረሳን አይችልም፡፡
 
ለዚህም አብነቶችን ማንሣት ይቻላል፡፡ በእንግሊዝ ሠራዊት የተዘረፈውን አንድን የመጾር መስቀል ፎቶ ግራፍ ለማንሳት ብቻ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠር ገንዘብ ቅርሱን በያዘው ክፍል መጠየቁ እንዲሁም የቅዱስ ላሊበላ አፍሮ አይገባ መስቀላችንን ከቤልጅም በከፍተኛ ዋጋ መግዛታችን የቅርብ ጊዜ ትዝታዎቻችን ናቸው፡፡
 
ይህ አልበቃ ብሎ ቅርሶቻችን ያለ አግባብ በሕገ ወጥ መንገድ ከሀገር እየወጡ በአሜሪካና አውሮፖ በመረጃ መረቦች አማካ ኝነት በግልጽ እየተቸበቸቡ ይገኛሉ፡፡ ዛሬም ቅርሶች የሚገኙባቸው አድባራት፣ ገዳማትና አብያት ክርስቲያናት፣ ተቋማት መካነ ቅርሶች መደፈራቸውና በውስጣቸው የሚገኙ ብርቅና ድንቅ ሃይማኖታዊ፣ ታሪካዊና ባሕላዊ ቅርሶች መዘረፋቸው አልተገታም፡፡
 
ቅርሶች ለጊዜያዊ አፍቅሮተ ንዋይ ሲባል ያለ አግባብ የመዘረፋቸው የመበላሽታቸውና የመባከናቸው መርዶ አልቆመም፡፡ ከዚህ አንፃር ይህ ወቅት ለእኛ ለአሁን ትውልድ ወጣቶች፣ ለቤተክርስቲያን አባቶችና ለመንግሥት ሁለት ሊታለፉ የማይችሉ ፈተናዎች ለምርጫ ከፊት ለፊታችን ተደቅነዋል፡፡ እነዚህ ምርጫዎች አንድም ቅርሳችንን ሕገ ወጥ ዝርፊያ ማስቆም፣ ያለ አግባብ የተዘረፉትን ለማስመለስ በተጀመረው ጥረት ሳይታክቱና ሳይሰለቹ መቀጠልና በእጃችን ያሉትን ጠብቆና ተንከባክቦ ለቤተክርስቲያን ዕድገትና ለሀገር ልማት እያመቻቹ ለተተኪው ትውልድ በማስተለለፍ ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ግዴታዎችን መውጣት፤ ወይም አሁን በአብዛኞቻችን እየተደረገ እንዳለው ዘረፋና ጥፋቱን በግዴለሽነት በመመልከት ድሀ ደካማና መረጃ አልባ ሀገር እና ቤተክርስቲያን ለትውልድ ጥሎ በማለፍ የታሪክና ትውልድ ተወቃሽ መሆን ናቸው፡፡
 
ያለ ማወላወል ለማንኛውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ አገልጋይ ካህናት እንዲሁም ሀገር ወዳድ እና ቅን ዜጋ ምርጫ ሊሆን የሚገባውና የሚሆነው የመጀመሪያው ነው፡፡ በመጀመሪያው ምርጫችን መሠረት ከመንግሥት ለቅርስ እንክብካቤ የሚጠበቀው ሚና ቅርሶችን ለመጠበቅ፣ ለመንከባከብና ለማልማት በርካታ ሕጐችን፣ አዋጆችንና ፖሊሰዎችን ማውጣቱንና ዓለም ዓቀፋዊ እና አህጉራዊ የቅርስ ስምምነቶችን መፈራረሙ ይታወቃል፡፡ ለምሳሌ በሕገ መንግሥቱ አንቀጸ 91 ላይ ስለ ቅርስ መደንገጉ የቅርስ ጥናትና አጠባበቅ አዋጅ መውጣቱ፣ የባሕል ፖሊሲ መቀረጹ እና ሀገሪቱ ቅርሱን አስመልክቶ ዓለም አቀፋዊ ስምምነቶችን መፈራረሟ የሚያሳየው መንግሥት ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት መስጠቱን ነው፡፡
 
ይሁን እንጂ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች መፈራረምና ሕጎችንና አዋጆችን ቢወጡም አሁን የሚታየውን የቅርስ ዘረፋ ቀጥሏል፡፡ በቅርስ ዘረፋ ተሰማርተው ለተያዙት ሰዎች የሚሰጠውም ቅጣት ለሌሎች አስተማሪ ባለመሆኑም ለዘራፊዎች መበራከት ተጠቃሽ ምክንያት ነው፡፡ የቅርስ ዘረፋን አስመልክቶ ቀድሞም ሆነ አሁን  ተሻሽለው የወጡት ሕጎችና አዋጆች ግን ጉዳዩን አስመልክተው ያወጡት የቅጣት ውሳኔ ከፍተኛ ነበር፡፡ በቅርስ ጉዳይ ላይ በወጡ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች የሚደረጉት ቅርሶች ከአንድ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር በሕገ ወጥ መንገድ እንዳይተላለፍ ለመከላከል በማሰብ ነው፡፡ ኢትዮጵያም እነዚህን ዓለም አቀፍ ስምምነቶች በመፈራረሟ በስምምነቱ  ተጠቃሚ ልትሆን ይገባት ነበር፡፡ ሀገራችን ከውጪ ወደ ውስጥ የምታስገባው ቅርስ ባይኖረም፤ ከእርሷ ግን ብዙ ቅርሶች በሕገ ወጥ መንገድ የተዘረፋት ቅርሶች ወደ የሀገራችው እንዳመለሱ ያዛል፡፡ ይሁን እንጂ ይህንን ጉዳይ ተግባራዊ ለማድረግ እና የተዘረፍብን ቅርሶችን ወደ ሀገር ለማስመለስ እየተደረገ ያለው ጥረት ጥሩ ቢሆንም በውጪ ካለን የቅርስ ብዛት አንፃር ሲመዘን ከቁጥር የሚገባ ባለመሆኑ በዚህ ረገድ የሕገ አስፈጻሚ አካላት ብዙ መሥራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ቅርሶችን አስመልክቶ የወጡት ሕጎች በትክክል እንዲፈጸሙ ገቢራዊ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
 
የቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አባቶች የእምነቱ ተከታዮች የቅርሰ ዘረፋን ሕገ ወጥ ዝውውርን ይበልጥ የመንከባ ከብና የመጠበቅ ግዴታ እንዳለብን ልናውቅ ይገባል፡፡ አሁን በሥራ ላይ ባለው አዋጅ ቁጥር 2ዐ9/1992 ዓ.ም ላይ የቅርስ ባለቤት የሆነ ሰው በእጅ የሚገኘውን ቅርስ ተገቢውን  ጠበቃና እንክብካቤ ካላደረገ… ለቅርሱ አጠባበቅ የሚወጡ ደንቦችንና መመሪያዎችን ያላከበረ እንደሆነ ወይም በይዞታው እንዲጠቀምበት በተሰጠው መሬት ላይ የሚገኝ ቅርስ በሚገባ የማይጠብቅ ከሆነ ወይም ቅርሱን የሚያሰተላልፍ ሰው የቅርሱን ማስተላለፍ ለባለስልጣኑ /ለመንግሥት/ ያላሳወቀ እንደሆነ… ይህን አስመልክቶ የወጣውን አዋጅ የማያስፈጸም ከሆነ እሰከ ስድስት ወር እስራት እንደሚቀጣና ወይም እስከ 1 ሺሕ አምስት መቶ ብር እንደሚቀጣ ተደንግጓል፡፡
 
በየጊዜው ትኩረት እየተሰጣቸው አዋጆች ገቢራዊ እንዲሆኑ  የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ክትትል ማድረግ አለባቸው፡፡ በቅድሚያ የአገራችን ሕዝብ ሁሉ የኢትዮጵያ መገለጫና የቱሪስት መስህብ የሆኑ ቅርሶች የአገራቸው ሀብት በመሆናቸው በባዕዳን ሲዘረፉ ሲቃጠሉ በቸልታ መመልከት የለባቸውም፡፡ ምእመናንም ቀደምት አበው ቀን በጽሕፈት ሌሊት  በጸሎት ተገተው ያዘጋጇቸው መጻሕፍት የገዳሟቸው ገዳማት ያካበቷቸው ንዋያተ ቅድሳት የእምነታቸው መገለጫ በመሆናቸው በእኔነት ስሜት ሊጠብቋቸው፤ ተዘርፈው ሲሄዱ ጥብቅና ሊቆሙላቸው ይገባል፡፡

የቅርስ ባለቤት የሆነችው ቅድስት ቤተክርስቲያን በየገዳማቱና አድባራቱ የሚገኙ ቅርሶቿን ሥርዐት ባለው መንገድ መመዝገ ብና ስለ ቅርሶቿ ተጨባጭ የሆነ መረጃ መስጠት አለባት፡፡ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋርም በመቀናጀት ቅርሶች ሲዘረፉ፣ ሲቃጠሉ በፍጥነት ለሕግ አስፈጻሚ አካላት ተገቢን እገዛ ማድረግ ይጠበቅባታል፡፡ ይኸውም ባለቤት በማጣት በግለሰቦችና በእግዚቢትነት ተይዞ የሚገኝ ቅርሶቿን ለማስመለሰ ይረዳታል፡፡
 
በአጠቃላይ ቅርሶች የሀገራችን ሀብታት የቀደሙት አበው ሥልጣኔ መገለጫ ዛሬ ላይ ቁጨ ብለን የትላንትን የምናይባቸው የክብራችን ገላጭ የእኛነታችን መለያ አሻራ በመሆናቸው በኅብረት እንክብካቤ ልናደርግላቸውና ጥብቅና ልንቆምላቸው ይገባል፡፡
የሕግ አስፈጻሚ አካላት ቢሆኑም በቅርስ ዙሪያ የወጡ ሕጎችንና አዋጆችን በትክክል መፈጸማቸውን ይከታተል፤ የቅርስ ዘረፋን እና ሕገወጥ ዝውውርን ለመግታት ሕጎች በትክክል ሊፈጸሙ ይገባል፡፡

 

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር