እግዚአብሔር የመረጠው ጾም

ለተወሰነ ሰዓት ከምግበ ሥጋ የመከልከላችን ዓላማ ራሳችንን መግዛት እንድንችል ነው፡፡ ስለዚህ ‘እየጾምኩ ነው’/የሚል ሰው ካለ ከምንም በፊት ትዕግሥተኛ ፣ ልበ ትሑትና የዋህ ፣ እግዚአብሔርን የሚፈራ ልቡና ያለው ፣ የፍትወታትን ጅረት ከኹለንተናው የሚያስወግድ ፣ ዘወትር በልቡናው ዕለተ ምጽአትን የሚያስብ ፣ በእግዚአብሔር የፍርድ ዙፋን ፊት እንደሚቆም የማይረሳ ፣ በፍቅረ ንዋይ ወጥመድ ተይዞ ምጽዋትን የማይጠላ፣ ወንድሙን ከልቡ የሚወድ ይኹን፡፡ እውነተኛ ጾም ማለት ይኽ ነውና፡፡

“ሰው ራሱን ቢያሳዝን ፣ አንገቱንም እንደ ቀለበት ቢያቀጥን ፣ ማቅ ለብሶ በአመድ ላይ ቢተኛም ይህ ጾም እግዚአብሔር ዘንድ የተመረጠ አይደለም” “ታዲያ እግዚአብሔር የመረጠው ጾም እንዴት ያለ ነው?” ትሉኝ እንደ ኾነም ነቢዩ ኢሳይያስ የእግዚአብሔር አፈ ንጉሥ ኾኖ እንዲህ ሲል ይመልስልናል፡

“የበደልን እስራት ፍታ ፡ ለተራበው እንጀራህን አጥግበው ፡ ድኾችን ወደ ቤትህ አስገብተህ አሳድራቸው ” እንዲህ ስታደርግ ፡- “ያን ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ይበራል፡፡ ፈውስህም ፈጥኖ ይወጣል” ትን.ኢሳ.58 ፥ 5-8

†ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ†

ምንጭ -ኦሪት ዘፍጥረት መፅሐፍ – በገብረ እግዚአብሔር ኪደ