የነቢያት ሀገራቸው ቤተ ልሔም ደስ ይበልሽ

ክፍል ሁለት

በዲ/ን ዐቢይ ሙሉቀን

ደስ ይበልሽ የተባለች ማን ናት?

ቤተ ልሔም

ደስ ይበልሽ፡ለሀገሪቱ ነው፡፡ በሀገሪቱ ሰዎችን መናገር ነው፡፡ ሰው በሀገሩ፣ ሀገሩ ደግሞ በሰው ይጠራል፡፡ ስለዚህ ቤተ ልሔም ሆይ ደስ ይበልሽ ፡፡ ምክንያቱም እስራኤልን የሚጠብቃቸው ንጉሥ ክርስቶስ ባንቺ ይወለዳልና፡፡ ሀገር ደግ ሰው ሲወለድበት፣ ደግ ሰው ሲወጣበት  ያስደስታል፡፡ አንዳንዴ “ሀገር ይባረክ” ተብሎ ይመረቃል፡፡ ሰው ይውጣበት ማለት ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ሀገርም በሰው ክፋት የተነሣ ሰው አይውጣብሽ ተብላ ልትረገም ትችላለች፡፡ በአዳም ምክንያት ምድር ተረግማለች፡፡ “እግዚአብሔር አምላክም አዳምን አለው የሚስትህን ቃል ሰምተሃልና ከእርሱ እንዳትበላ ካዘዝኩህ ከዚያ ዛፍም በልተሃልና ምድር በሥራህ የተረገመች ትሁን፤ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ እሾኽንና አሜከላን ታበቅልብሃለች፤ የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡” (ዘፍ.፫፥፲፯-፲፰፡፡) ነገር ግን ከዚህ መርገም ድኖ ደግ ሰው ማስገኘት ያስደስታል፡፡ ይልቁንም ቤተ ልሔም እስራኤልን የሚያድናቸው አምላክ፣ የሚጠብቃቸው እውነተኛ እረኛ፣ እነሆ “እስራኤልን የሚጠብቀው አይተኛም፣ አያንቀላፋምም”  (መዝ.፻፳፥፬) እንዲል፤ የሚታደጋቸው መሓሪ አምላክ ነው የተወለደባትና፣ ደስ ይበልሽ ተብላለች፡፡

ቤተ ልሔም ሀገሮሙ ለነቢያት ተብላለች፡፡ ነቢያት ትንቢት ተናግረውባታልና፡፡ የተናገሩት ትንቢት፣ የቆጠሩት ሱባኤ ሲፈጸም ትንቢቱ ለተነገረባት ለሀገሪቱም፣ ትንቢቱን ለተናገሩት ነቢያትም ታላቅ ደስታ ነውና ሀገሮሙ ለነቢያት ተብላለች፡፡ ደግ ነገር በተፈጸመት ሀገር ኖሮ ሀገሪቱ የእነገሌ ናት ሲባል ሰዎችን ያስደስታል፡፡ ሀገሪቱንም የእነገሌ ሀገር ማስባል እጅግ ኩራትን ያሰጣልና ሀገሮሙ ለነቢያት ተብላ ተጠራች፡፡ ሀገሮሙ ለነቢያት ከተባለላቸው ከእነዚህ ነቢያት መካከል ዳዊትና ሚክያስ ይገኙበታል፡፡

ዳዊት ቤተ መቅደሱን ለመሥራት ሲሻ ለነቢዩ ናታን እንዲህ ብሎ ነገረው፡፡ “እኔ ከዝግባ በተሠራ ቤት ተቀምጫለሁ፤ የእግዚአብሔር ታቦት ግን በድንኳን ውስጥ ተቀምጣለች” አለው፡፡ ናታንም ንጉሡን “እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነውና ሂድና በልብህ ያሰብኸውን ሁሉ አድርግ” አለው፡፡ በዚያም ሌሊት የእግዚአብሔር ቃል ወደ ናታን እንዲህ ሲል መጣ፤ እንዲህም አለው፡- “ሒድ ለባሪያዬ ለዳዊት ንገረው እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ አንተ የምኖርበትን ቤት አትሠራልኝም፡፡” (፪ሳሙ.፯፥፪-፭) አለው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ለዳዊት ድንቅ የሆነው የደገኛው ነገር የነገረ ድኅነት ምሥጢር ተገልጾለት “ናሁ ሰማዕናሁ በኤፍራታ ወረከብናሁ ውስተ ዖመ ገዳም፤ እነሆ በኤፍራታ ሰማነው፣ ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው፡፡” (መዝ.፻፴፩፥፯) በማለት ተናገረ፡፡ ስለዚህ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የምሥጢረ ሥጋዌ ነገር ተገልጾለት ትንቢት የተናገረባት ቦታ ስለሆነች ሀገሮሙ ለነቢያት ተብላለች፡፡

ሁለተኛው ደግሞ ሚክያስ ነው፡፡ ይህ ነቢይ ሲያስተምር ውሎ ማታ በዚህች በቤተ ልሔም በኩል ሲመለስ እስራኤላውያን በባቢሎናውያን ተማርከው ቤተ ልሔም ምድረ በዳ ሆና ተመለከታት፡፡ በዚህ ጊዜ “እነሆ የጽዮንን ሴት ልጅ ከበው ያጥሯታል፤ የእስራኤልንም ወገኖች ጉንጫቸውን በበትር ይመታሉ፡፡ አንቺም የኤፍራታ ምድር ቤተ ልሔም ሆይ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ነገር ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘለዓለም የሆነ በእስራኤል ላይ ገዥ የሚሆን ከአንቺ ይወጣልኛል፡፡ ስለዚህ ወላዲቱ እስከምትወልድበት ጊዜ ድረስ አሳልፎ ይሰጣቸዋል፤ የቀሩትም ወንድሞቻቸው ወደ እስራኤል ልጆች ይመለሳሉ፡፡” (ሚክ.፭፥፩-፬) በማለት ለጊዜው እስራኤላውያን ተማርከው እንደማይቀሩ በዘሩባቤል መሪነት በእግዚአብሔር ቸርነት ተመልሰው ወደ ርስታቸው እንደሚገቡ ተናግሯል፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ሚክያስ ለጊዜው እስራኤል ዘሥጋን ያጣች ቤተ ልሔም ምድረ በዳ እንደሆነች፡፡ በዚህ ምድረ በዳነቷም እንደማትቀጥል እስራኤል ከምርኮ ተመልሰው እንደሚሰፍሩባት፣ እንደሚደሰቱባት፣ ንጉሥ ዘሩባቤል እንደሚነግሥባት ተናገረ፡፡ እንዲሁም ሆነ፡፡ እስራኤል ከምርኮ ተመለሱ፤ ተደስተውም ዘመሩባት፡፡ ፍጻሜው ግን እስራኤል ዘነፍስን ያጣች ገነት የሚገባባት አጥታ ባዶ እንደሆነች፣ ነገር ግን እስራኤልን የሚጠብቅ ንጉሥ ክርስቶስ ከጠላት የሚያድን አምላክ እንደሚወለድባት ያስረዳል፡፡ በመሆኑም ቤተ ልሔም ንጉሠ ሰማያት ወምድር አምላክ ተወልዶባት መላእክት ዘመሩባት፤ ሰውና መላእክት ታረቁባት፤ የእስራኤል ነጻነት ታወጀባት፡፡ “እነሆ ለእናንተና ለሕዝቡ ሁሉ ደስታ የሚሆን ታላቅ የምሥራችን እነግራችኋለሁና አትፍሩ አላቸው፡፡” (ሉቃ.፪፥፲) ተብሎ ተነገረባት፡፡

ለዚህም ነው ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም “ስለ ክርስቶስ ባንድ መንፈስ ቅዱስ ትንቢት የተናገሩት የእነዚህ የሚክያስና የዳዊት ነገር ምን ይደንቅ” (ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ) በማለት የተናገረው፡፡ እውነት ነው የተነገረው ትንቢት በመንፈስ ቅዱስ መሆኑን እንድንረዳ አንድ ዐይነት ትንቢት ግን በተለያየ ጊዜ በተለያዩ ሰዎች ተነገረ፡፡ ደግሞ የተነገረው ትንቢት፣ የተቆጠረው ሱባኤ ሲፈጽም የአናገረው መንፈስ ቅዱስ መሆኑን የተናገሩት ነቢያት ደግሞ ደጋግ መሆናቸውን የሚያስረዳ ነውና የእነሱም ነገር ምን ይደንቅ ተባለ፣ ሀገሪቱም ከዚህ የበለጠ ደስታ ስለሌለ ደስ ይበልሽ ተባለች፡፡

እመቤታችን

ድንግል ማርያም የነቢያት ሀገራቸው ደስ ይበልሽ ተብላለች ፡፡ ለምን የነቢያት ሀገራቸው ተባለች ከተባለ የአበው ሱባኤና ተስፋ፣ የነቢያት ትንቢት በእርሷ ስለተፈጸመ ነው፡፡ ለዚህም ነው “ትንቢቶሙ ለነቢያት፣ እሞሙ ለሰማዕት፣ ወእህቶሙ ለመላእክት” የምትባለው፡፡  የነቢያት ትንቢት በእርሷ ስለ ተፈጸመ “ትንቢቶሙ ሀገሮሙ ለነቢያት” ተብላለች፡፡ በተጋድሎ፣ በስደት፣ በመከራ ወዘተ ስለምትመስላቸው “እሞሙ ለሰማዕት፣ የሰማዕት እናታቸው” ተብላለች፡፡ በንጽሕና፣ በቅድስና ስለምትመስላቸው ደግሞ “እህቶሙ ለመላእክት፣ የመላእክት እህታቸው” ተብላለች፡፡ ቤተ ልሔምን እና ድንግል ማርያምን የሚያመሳስላቸው ነገር ምንድን ነው? ቢባል የቤተ ልሔምን ከላይ በገለጽነው መንገድ መረዳት ይቻላል የድንግል ማርያምን ደግሞ እንደሚከተለው እንመልከት፡፡

“ኦ ከርሥ ዘተጽሕፈ ውስቴታ መጽሐፈ ግእዛን እምግብርናት ለኩሉ ሰብእ፤ ኦ ከርሥ  ዘተረጸውረ ውስቴታ ንዋየ ሐቅል ዘይትቃወሞ ለሞት በእንቲኣነ፤ ለሰው ሁሉ ከመገዛት የነጻነት መጽሐፍ የተጻፈባት ማሕፀን እንደምን ያለች ናት፣ ስለኛ ሞትን የሚቃወም ክርስቶስን የተሸከመች ማኅፀን ወዮ እንደምን ያለች ናት፡፡” (ሃ/አበ.፵፰፥፲፭) በማለት ሊቁ ቅዱስ ኤራቅሊስ በሃይማኖተ አበው ነገረ ሥጋዌን በተናገረበት አንቀጹ ተናገረ፡፡

ይህ ለሁሉ የነጻነት መጽሐፍ የተጻፈባት የተባለች ጥንት በትንቢተ ኢሳይያስ እንዲህ ተብላ ተገልጻለች፡፡ “ደከሙ፤ ደነገጡ፤ ሰከሩም፤ በወይን አይደለም፤ በጠጅም አይደለም፡፡ እግዚአብሔር የእንቅልፍ መንፈስን አፍሶባቸዋል፤ ዐይኖቻቸውን የነቢያትንም ዐይን የተሰወረውንም የሚያዩ የአለቆቻቸውን ዐይን ጨፍኖባቸዋል፡፡ ይህም ሁሉ ነገር እንደታተመ መጽሐፍ ቃል ሆኖባቸዋል፤ ማንበብንም ለሚያውቅ “ይህን አንብብ” ብለው በሰጡት ጊዜ እርሱ ታትሟልና “ማንበብ አልችልም” ይላቸዋል፤ ደግሞም መጽሐፉን ማንበብ ለማያውቅ “ይህን አንብብ” ብለው በሰጡት ጊዜ “ማንበብ አላውቅም” ይላቸዋል፡፡ (ኢሳ.፳፱፥፱)፡፡

ከላይ በተገለጸው ምንባብ በርካታ ሐተታዎች ቢኖሩትም ከዚህ ርእስ ጋር የሚሄደውን ብቻ ለማየት እንሞክራለን፡፡ የታተመ መጽሐፍ የተባለች ድንግል ማርያም፣ ማንበብ የማይችል  የተባለ ዮሴፍ፣ ማንበብ የሚችል የተባለው ሚስቱን በግብር የሚያውቅ ማለት ነው፡፡ ማንበብ የማይችል የተባለ ደግሞ ድንግል ማርያምን በግብር የማያውቅ ማለት ነው፡፡ በድንግልና ፀንሳ በድንግልና መውለዷ ጭንቅ ይሆኖበታል፡፡ “ኢያእመራ ዮሴፍ እስከ አመ ወለደት ወልደ ዘበኲራ፤ የበኲር ልጇን እስከ ወለደች ድረስ አላወቃትም” እንዲል፡፡ እስከ የሚለውንም ቃል ፍጻሜ የሌለው እስከ እንደሆነ ልብ ይሏል፡፡ ሜልኮል እስከ ሞተችበት ጊዜ ድረስ አልወለደችም ይላል፤ ከሞተች በኋላ ወለደች ማለት አይደለም ፍጻሜ የሌለው እስከ ነው እንጂ፡፡ ኖኅ የላከው ቁራም የጥፋት ውኃ እስከ ጎደለ ድረስ አልተመለሰም ይላል፤ ከዚያ በኋላ ተመለሰ የሚል ታሪክ አልተጻፈም ፍጻሜ የሌለው እስከ ነው እንጂ፡፡

እንዲሁም መጽሐፍ ማንበብ የሚያውቅ የተባለ ዮሴፍ ሚስቱን በግብረ ሥጋ የሚያውቅ፣ መጽሐፍ እንደታተመ ሰጡት፣ አልተገለጠምና ማንበብ አልቻለም፡፡ መጽሐፍ የተባለች ድንግል ማርያም እንደ ታተመች ሰጡት ማንበብ አልቻለም፡፡ አይሁድ በቅንዓት ከቤተ መቅደስ ሲያስወጧት ከእግዚአብሔር አግኝተን እንደ ሰጠንህ ከእግዚአብሔር አግኘንተን እስክንቀበልህ ድረስ ጠብቅ ተብሎ ተሰጥቷልና፡፡ እንደ ታተመ ሰጡት ግን ማንበብ አልቻለም ተባለ፡፡ ማኅተመ ድንግልናዋን እንደ ጠበቀች እንድትኖር እንጂ በግብር ሊያውቃት አይደለምና፡፡

ማንበብ ለማይችለው የተዘረጋ መጽሐፍ ሰጡት ግን ማንበብ አልቻለም፡፡ ማንበብ ስለማይችል ነገረ ሥጋዌ በአበው ምሳሌ፣ በነቢያት ትንቢት ሲነገር የኖረና በተስፋ ሲጠበቅ የኖረ ነው፡፡ ግን ማንበብ ለማይችል ሰጡት አለ፡፡ ይህ ትንቢት የተነገረው ለማን እንደሆነ ላላወቀው ዮሴፍ ሰጡት ማንበብ አልቻለም፡፡ ድንግል የተባለች እርሷ፣ ወልድ የተባለ ከእርሷ የሚወለደው ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፣ አበው ምሳሌ የመሰሉለት እርሱ እንደሆነ አላወቀም ነበር፡፡ ስለዚህ ማንበብ አልቻለም ተባለ፡፡

ይህም ነገር ዮሴፍን እጅግ አስጨነቀው ሊቁ ኤራቅሊስ እንደሚነግረን “የድንግል ሆዷ ገፋ፣ ያለ ዘር የፀነሰች የድንግልን የሆድዋን መግፋት ባየ ጊዜ የዮሴፍ ልቡ አዘነ፤ የንጽሕት እመቤታችንን ምሥጢሯን ፈጽሞ መረመረና በማያውቀው ምሥጢር ፀንሳ ቢያገኛት በጽኑእ ሐሳብ በማውጣት በማውረድ ተያዘ” (ሃ/አበ.፵፰፥፴፫) እንዲል፡፡ ነገሩ አምላካዊ ነውና ዮሴፍ ማወቅ አልቻለም፡፡ ባለማወቁም ተጨነቀ፡፡ ለዚህ ነው ማንበብ ለማያውቅ መጽሐፍ ሰጡት ግን ማንበብ አልቻለም፣ ያልተማረ ማንበብ የማያውቅ ነውና የተባለው፡፡

ሌላው መጽሐፍ የተባለ መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ማንበብ የሚችል፣ ማንበብ የማይችል የተባሉ አይሁድ ናቸው፡፡ ማንበብ የሚችል ማለት ትንቢት የተነገረላቸው፣ ሱባኤ የተቆጠረላቸው በሕገ ኦሪት የሚመሩ የመሢሁን መምጣት የሚጠባበቁ ስለሆኑ ነው፡፡ ማንበብ የማይችል የተባሉት ሲጠባበቁት የነበረው መሢህ ትንቢቱን ሊፈጽም እነሱን ሊያድን ቢመጣ አልተቀበሉትም፡፡ ያ ትንቢት የተነገረለት፣ ሱባኤ የተቆጠረለት እርሱ እንደሆነ አምኖ መቀበል አለመቻላቸው ነው፡፡ ማንበብ ለሚችል የታጠፈ መጽሐፍ ሰጡት የተባለ ትንቢቱ የተነገረልን፣ ሱባኤው የተቆጠረልን እኛ ነን ለሚሉት ግን የታተመ መጽሐፍ ተሰጣቸው እነሱ በሚያስቡት መንገድ አለመገለጡን ሲያስረዳ ነው፡፡ እነሱ የሚያስቡት ብዙ ሠራዊት አስከትሎ፣ የጦር መሣሪያ አስይዞ ከሮማውያን ግዛት ነጻ የሚያወጣ ነበርና፡፡

ማንበብ ለማይችለው የተገለጠ መጽሐፍ ተሰጠው ግን ማንበብ ስለማይችል አላነበበውም የተባለው ደግሞ አምላክነቱን የሚያስረዱ በርካታ ተአምራትን እያደረገ ሕሙማንን እየፈወሰ፣ ሙታንን እያስነሳ ዕዉራንን እያበራ እኔ አምላክ ነኝ ቢላቸው አላመኑበትም፡፡ ምክንያቱም ማንበብ አይችሉምና፣ ማለት ሃይማኖት የላቸውምና፡፡ እርሱ ደግሞ የሚታወቅ በሃይማኖት ስለሆነ፡፡ “በሃይማኖት ነአምር ከመ ተፈጥረ ዓለም በቃለ እግዚአብሔር፤ ዓለም በእግዚአብሔር ቃል እንደ ተፈጠረ በሃይማኖት እናውቃለን፡፡” በማለት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ነው፡፡

ለምን ደስ ይበልሽ አላት

የዚህ ሁሉ ምሥጢር መፈጸሚያ መዝገብ ሆናለችና ተፈሥሒ፤ ደስ ይበልሽ አላት፡፡ ከመልአኩ ከቅዱስ ገብርኤል እንደተረዳው እንዲህ በማለት “እስመ እምኔኪ ይትወለድ ክርስቶስ ዘይርዕዮሙ ለሕዝብየ እስራኤል፤ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቃቸው ክርስቶስ ከአንቺ ይወለዳልና፡፡” ሰዎች በተለይም እናቶች ልጅ ወልዶ እንደ ማሳደግ ደስ የሚላቸው ነገር የለም፡፡ ስለዚህም አንዲት እናት ልጅ ስትወልድ እንኳን ደስ አለሽ፣ እንኳን ማርያም ማረችሽ ትባላለች፡፡ ሴቶች ልጅ ትወልዳላችሁ ሲባሉ ደስ ይላቸዋል፤ ይልቁንም ወንድ ልጅ ትወልዳላችሁ ሲባሉ  እጅግ ደስ ይላቸዋል፡፡ ድንግል ማርያም በብሥራተ መልአክ የተነገረችው የዓለሙን መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስን ነውና መልአኩም ደስ ይበልሽ ብሏታል፡፡ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትን፣ ሐዋርያትን የወለዱ እናቶችም ደጋግ ልጆች በመውለዳቸው ይከበራሉ፤ ይመሰገናሉ፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ደግሞ የወለደችው ዓለሙን ያዳነውን ጌታ ነውና ደስ ይበልሽ ልትባል ይገባታል፡፡

ለምን ተወለደ?

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የሆነበት ሁለት መሠረታዊ ዓላማዎች አሉት፡፡ አንደኛውና ዋነኛው ሰውን ለማዳን ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ለአርአያነት ነው፡፡ አርአያነቱንም የደቀ መዛሙርቱን እግር አጥቦ ትሕትናን፣ ለሚያሰቃዩት ጸልዮ ፍቅርን፣ ወዘተ በመግለጽ አሳይቷል፡፡ ሰውን ለማዳን እንደመጣም ሊቁ ሰው የሆነበትን ምክንያት ሲገልጥ “ልቡ የአዘነና የተከዘ አዳምን ወደቀደመ ቦታው ይመልሰው ዘንድ ወደደ” ነው ያለን፡፡  ወደ ቀድሞ ክብሩ ልጅነት፣ ወደ ቀድሞ ቦታው ገነት ይመልሰው ዘንድእስመ በኀቤኪ ተወልደ ክርስቶስ ዳግማይ አዳም ከመ ያግብኦ ለአዳም ቀዳሚ ብእሲ እምድር ውሰተ ገነት፤ ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ አዳምን ከሲኦል ወደ ገነት ይመልሰው ዘንድ በአንቺ ተወልዷልና ደስ ይበልሽ” አለ፡፡

አዳም ከገነት ተባሮ ስደተኛ ሆኖ ነበርና ባለ ርስት ባለ ጉልት ሊያደርገው ሰው ሆኖ በሥጋ አዳም ተገለጠ፡፡ በመሆኑም በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት የመንግሥቱ ወራሾች ሆን፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እምይእዜሰ ኢኮንክሙ ነግደ ወፈላሴ አላ ሰብአ ሀገሪቶሙ ለቅዱሳን ወሰብአ ቤቱ ለእግዚአብሔር፤ እንግዲህስ ወዲህ እናንተ ከቅዱሳን ጋር ባለ ሀገሮችና የእግዚአብሔር ቤተሰቦች እንጂ እንግዶችና መጻተኞች አይደላችሁም፡፡” (ኤፌ.፪፥፲፱) በማለት እንደገለጸልን ወደ ርስቱ ይመልሰው ዘንድ ሰው ሆነ፡፡ ስለዚህ ንጉሥ ክርስቶስ ሰውን ወደ ርስቱ ይመልሰው ዘንድ ካንቺ ተወልዷልና ደስ ይበልሽ ተባለች፡፡

በአጠቃላይ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም ተፈሥሒ ኦ ቤተ ልሔም ሀገሮሙ ለነቢያት ያላት ለጊዜው ነቢያት ያመሰገኗትን ቤተ ልሔምን ሲሆን፤ ፍጻሜው ግን የነቢያት ትንቢትም ፍጻሜውን ያገኘው በድንግል ማርያም ስለሆነ ድንግል ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ እያለ አመሰገናት፡፡ ለምን አመሰገናት ከተባለ ደግሞ የአምላክ እናት ስለሆነች፡፡ እኛም እንደ ሊቃውንቱ ድንግል ማርያምን አመስግነን ከድንግል ማርያም በረከት እንድናገኝ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የመላእክት ጥበቃ፣ የቅዱሳን ሁሉ ተራዳኢነት አይለየን አሜን፡፡

የነቢያት ሀገራቸው ቤተ ልሔም ደስ ይበልሽ

ክፍል አንድ

ዲ/ን ዐቢይ ሙሉቀን

የቃሉ ተናጋሪ የሶርያው ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ በአበው የተመሰለው ምሳሌ፣ በነቢያት የተነገረው ትንቢት ፍጻሜውን ያገኘው በድንግል ማርያም እና ለአዳም የገባውን ቃል ኪዳንና ትንቢተ ነቢያትን ሊፈጽም ወደዚህ ዓለም በመጣው በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ስለዚህ የትንቢተ ነቢያት መፈጸሚያ የሆነችውን ድንግል ማርያምን ባመሰገነበት ድርሰቱ ተናግሮታል፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም በሰኞ ውዳሴ ማርያም ድንግል ማርያምን በቀጥታ ስሟን አልጠራም፡፡ የድርሰት ትኩረቱም መከራ አዳምና ድኅነተ አዳም (ነገረ ድኅነት) ላይ ነበር፡፡ በመሆኑም ይህ ነገረ ድኅነት በደጋግ አባቶችም፣ በነቢያትም፣ በብዙ ቅዱሳንም እንዳልተፈጸመ በድንግል ማርያም ብቻ እንደተፈጸመ ይገልጻል፡፡ እንዲያውም አዳምንና ሔዋንን አስከትላ መጥታ ነበርና ቢያያቸው አነሣቸው፡፡ እንዲህ በማለት “ጌታ ልቡ ያዘነና የተከዘ አዳምን ነጻ ያወጣውና ወደ ቀድሞ ክብሩ ይመልሰው ዘንድ ወደደ፡፡” በማለት፤ አዳምን እንዳነሣ ሁሉ “ሠምረ ልቡ ኀበ ፍቅረ ሰብእ ወአግዓዛ፤ ሰውን ወደደና ነጻ አደረጋት” በማለት ደግሞ ሔዋንን ጠቀሰ፡፡

ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም አመስግነኝ ባለችው ጊዜ እሷን ከማመስገን አስቀድሞ ልጇ አዳምንና ሔዋንን ነጻ እንዳወጣ ይህንም ነጻ የማውጣት ሥራ ለመሥራት በራሱ ፈቃድ እንደሆነ እንዲህ ያለው ድንቅ ምሥጢር የተፈጸመባት ምሥጢራዊት ሀገር ደግሞ ድንግል ማርያም እንደሆነች ያስረዳል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርቶስ አዳምንና ሔዋንን ነጻ ለማውጣት በወደደ ጊዜ ነቢያት በመሰሉት ምሳሌ፣ በተናገሩት ትንቢት፣ ስማቸው የተጠቀሰውን ቅዱስ ኤፍሬም እያነሣሣ ሲያመሰግን ቤተ ልሔምንም አነሣት፡፡

ይህች ቤተ ልሔም ሙሴ፣ ኢያሱና ካሌብን ምድረ ርስትን ሰልላችሁ ኑ ብሎ በላካቸው ጊዜ ቤተ ልሔምን የእርሱ እንድትሆን ካሌብ ኢያሱን ለምኖት ነበር፡፡ ምድረ ርስትን ከወረሱ በኋላ ለካሌብ ሆናለች፡፡ በዚህ ጊዜ ከብታ የምትባል ሚስት አግብቶ በሚስቱ ስም ከብታ ተብላለች፡፡ ከብታ ልጅ ሳትወልድለት ቀረች፡፡ ኤፍራታ የምትባል ሚስት አግብቶ በሚስቱ ስም ኤፍራታ ብሎ አስጠርቷታል፡፡ ይህች ኤፍራታ ልጅ ወለደችለት፡፡ ሀብታቸው በዝቶላቸው ነበርና ልሔም አለው፡፡ ልሔም ማለት፡- ኅብስት፣ እንጀራ፣ ሀብት ማለት ነው፡፡ ልጁ አድጎ ፍርድ የሚጠነቅቅ፣ አስተዋይና ለተራበ የሚያበላ አዛኝ ሆነ፡፡ በእርሱም ቤተ ልሔም ተብላ ተጠርታለች፡፡ ይህም ስም ጸንቶላት ኖሯል፡፡

ከብታ፡- ከብታ ማለት ቤተ ስብሐት፤ የምስጋና ቤት ማለት ነው፡፡ ቤት የእመቤታችን፣ ስብሐት የጌታ ምሳሌ ነው፡፡ ምስጋና የባሕርዩ የሆነ አምላክ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ማሕፀኗን ዙፋን አድርጎ ተወልዷና የምስጋና ቤት ተባለች፡፡ ጌታን ፀንሳ ሳለ መላእክት በማሕፀኗ ያለውን ፈጣሪ ያመሰግኑት ነበርና የምስጋና ቤት ተባለች፡፡ እሷም ገና በሦስት ዓመቷ ቤተ መቅደስ ገብታ የመላእክትን ምስጋና ገንዘብ አድርጋ ዐሥራ ሁለት ዓመት ከመላእክት ጋር ፈጣሪዋን እያመሰገነች ኖራለችና የምስጋና ቤት ተብላለች፡፡ “ኦ መቅደስ ዘኮነ ባቲ እግዚአብሔር ካህነ፤ እግዚአብሔር ካህን ሆኖ ላገለገለባት መቅደስ አንክሮ ይገባል፡፡” (ሃ/አበው ፵፰፥፲፯) በማለት ሊቁ ኤራቅሊስ እንዳመሰገናት ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦባታልና የምስጋና ቤት ተብላለች፡፡

ሊቁ አባ ሕርያቆስም “ኦ ድንግል አኮ ወራዙት ስፉጣን ዘናዘዙኪ አላ መላእክተ ሰማይ ሐወጹኪ በከመ ተብህለ ካህናት ወሊቃነ ካህናት ወደሱኪ፤ ድንግል ሆይ የሚያታልሉ ጎልማሶች ያረጋጉሽ አይደለም፣ የሰማይ መላእክት ጎበኙሽ እንጂ፣ እንደተነገረ ካህናትና የካህናት አለቆች አመሰገኑሽ እንጂ፡፡” /ቅዳሴ ማርያም/ በማለት ምስጋና ያልተለያት፣ የምስጋና ቤት እንደሆነች አስረድቷል፡፡

     ኤፍራታ፡- ኤፍራታ ማለት ጸዋሪተ ፍሬ፤ ፍሬን የተሸከምሽ ማለት ነው፡፡ ጸዋሪት የእመቤታችን ፍሬ የጌታ ምሳሌ መልካም ፍሬ ከመልካም እንጨት ይገኛል፡፡ ባለቤቱ መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራል፤ ክፉ ዛፍም ክፉ ፍሬን ያፈራል፡፡” (ማቴ ፯፥፲፯) በማለት እንዳስተማረን መልካም ፍሬ የሚገኘው ከመልካም ዛፍ ነው፡፡ በመሆኑም ንጽሕተ ንጹሓት፣ ቅድስተ ቅዱሳት ኅጥዕተ አምሳላት ድንግል ማርያም የሕይወት ፍሬን ተሸክማ ለዓለም አድላለች፡፡ ስለሆነም ኤፍራታ፣ ጸዋሪተ ፍሬ ተብላ ትጠራለች፡፡

“አብርሂ፣ አብርሂ ናዝሬት ሀገሩ ንጉሥኪ በጽሐ ዘምስለ ማርያም መጾሩ፤ አንቺ ናዝሬት ሀገሩ አብሪ፣ አብሪ ንጉሥሽ ክርስቶስ ከመጾሩ (ተሸካሚው) ማርያም ጋር ደርሷልና” በማለት የፍሬ ሕይወት ጌታ ዙፋን የተባለች ድንግል ማርያም መሆኗን አባ ጽጌ ድንግል ነግሮናል፡፡ “ይጸውር ድደ ወይነብር ጠፈረ አኃዜ ዓለም በእራኁ ኲሉ እኁዝ ውስተ እዴሁ፤ በሰማያት ተቀምጦ መሠረትን ይሸከማል፤ ዓለምን በመሐል እጁ የሚይዝ ሁሉ በእጁ ያለ” /ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ/ የተባለለት ጌታ በአንዲት ብላቴና በድንግል ማርያም ማኅፀን ተወሰነ፡፡ እርሷም ጌታን ተሸከመችው ተባለ፡፡ ይህ ሁሉ ያስደነቀው ቅዱስ ያሬድም በድጓው “ሰማይ ወምድር ዘኢያገምሮ እፎ እንጋ ማኅፀነ ድንግል ጾሮ፤ ሰማይና ምድር የማይችለውን እንዴት የድንግል ማርያም ማኅፀን ቻለው” እያለ በአድናቆት ይነግረናል፡፡

እንዲሁም ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ በሃይማኖተ አበው “መኑ ርእየ ወመኑ ሰምዐ እስመ እግዚአብሔር ዘኢይትገመር ተገምረ በከርሠ ብእሲ ዘኢይጸውርዎ ሰማያት ኢያጽዐቆ ከርሣ ለድንግል አላ ተወልደ እምኔሃ እንዘ ኢይትዌለጥ መለኮቱ ወኢኮነ ዕሩቀ እመለኮቱ፤ የማይወሰን እግዚአብሔር በድንግል ማሕፀን እንደተወሰነ ማን አየ? ማን ሰማ? ሰማያት ለማይወስኑት እርሱ የድንግል ማሕፀን አልጠበበውም፣ ባሕርዩ ሳይለወጥ ከእርሷ ተወለደ እንጂ ከመለኮቱ የተለየ ዕሩቅ ብእሲ አይደለም፡፡” /ሃ.አበ.፷፮፥፭/ በማለት ማሕፀኗን ዙፋን አድርጎ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ እንደ ተወለደ ዙፋኑ ማደሪያው እንደ ተባለች ያስረዳናል፡፡

ፍሬ የተባለው ጌታ ነው፣ ያውም የሕይወት ፍሬ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በአንቀጸ ብርሃን ድርሰቱ እንዲህ ይለናል፡፡ “አንቲ ውእቱ ዕፅ ቡሩክ ዕፀ ሕይወት ወዕፀ መድኃኒት ህየንተ ዕፀ ሕይወት ዘውስተ ገነት ዘኮንኪ ዕፀ ሕይወት በዲበ ምድር ፍሬኪኒ ፍሬ ሕይወት ውእቱ ወዘበልዐ እምኔሁ ሕይወተ ዘለዓለም የሐዩ፤ አንቺ የተባረክሽ ዕፅ ነሽ፣ የሕይወትና የደኅንነት ዕፅ ነሽ፣ በገነት ውስጥ ባለው ዕፀ ሕይወት ፈንታ በዚህ ዓለም የሕይወት ዕፅ ሆንሽ፣ ፍሬሽም የሕይወት ፍሬ ነው፤ ከእርሱም የሚበላ ለዘለዓለም ይኖራል፡፡” እንዲል፡፡

ቤተ ልሔም፡- ቤተ ልሔም ማለት ቤተ ኅብስት ማለት ነው፡፡ ቤት የእመቤታችን፣ ኅብስት የጌታ ምሳሌ ነው፡፡  በቤት ብዙ ነገር ይገኛል፣ እርሷም ሁሉን ለሚችል ጌታ መገኛ ናትና፡፡ በቤት ውስጥ ከሚገኙት መካከል ምግብ አንዱ ነው፡፡ ድንግል ማርያምም የምግበ ሕይወት ጌታ መገኛ ናት፡፡ ሊቁ አባ ሕርያቆስ “ኦ ማርያም በእንተ ዝ ናፈቅረኪ ወናዐብየኪ እስመ ወለድኪ ለነ መብልዐ ጽድቅ ዘበአማን ወስቴ ሕይወት ዘበአማን፤ ማርያም ሆይ ስለዚህ እንወድሻለን፣ ከፍ ከፍም እናደርግሻለን፣ እውነተኛውን መብል፣ እውነተኛውን መጠጥ አስገኝተሽልናልና፡፡” በማለት በቅዳሴው ያመሰግናታል፡፡

ኅብስት የተባለ ጌታ ነው፡፡ “ከሰማይ  የወረደ ኅብስት እኔ ነኝ፤ ከዚህ ኅብስት የሚበላ ለዘለዓለም ይኖራል፤ ስለ ዓለም ሕይወት የምሰጠው ይህ ኅብስት ሥጋዬ ነው፡፡” (ዮሐ.፮፥፶፩) በማለት ራሱ ባለቤቱ መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ስብከቱ እንደነገረን፤ ኅብስት ያውም ሰማያዊ ኅብስት፣ ያውም ዘለዓለማዊ ሕይወትን የሚያድለው ኅብስት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ይህ ኅብስት ደግሞ ከድንግል ማርያም የነሣው ሥጋ ስለሆነ ድንግል ማርያም ቤተ ኅብስት ተብላለች፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምም “አንቲ ውእቱ መሶበ ወርቅ ንጹሕ እንተ ውስቴታ መና ኅቡእ ኅብስት ዘወረደ እምሰማያት፤ የተሠወረ መና ያለብሽ ንጹሕ የወርቅ መሶብ አንቺ ነሽ፣ መናም ከሰማይ የወረደው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡” (ውዳሴ ማርያም ዘእሑድ) በማለት እንደተረጎመልን የተሠወረ መና የተባለው ባሕርዩ የማይመረመር ኢየሱስ ክርስቶስ፣ መሶበ ወርቅ የተባለች ደግሞ ድንግል ማርያም ናት፡፡ ስለዚህ ለዚህ ለተሠወረው መና መገኛ ቤተ ኅብስት ድንግል ማርያም ናት፡፡

ይቆየን፡፡

“የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ” (፩ኛዮሐ. ፫፥፰)

መ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ  “የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ” በማለት የመሰከረው የመገለጡን ምክንያትም አያይዞ በመጥቀስ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ይህንን ምስክርነት የሰጠውም ስለ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

ከዓለም አስቀድሞ ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ የተወለደ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሆነ ከሦስቱ አካል አንዱ ወልድ በተለየ አካሉ በባሕርይ አባቱ በአብ፣በባሕርይ  ሕይወቱ  በመንፈስ  ቅዱስ፣በራሱም  ፈቃድ  ለድኅነተ  ዓለም  ከድንግል ማርያም በሥጋ እንደተወለደ እንረዳ ዘንድ ነው፡፡ በዚህም ቅድመ ዓለም ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት በመወለዱ ድኅረ ዓለም ከእናታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ያለ አባት በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንደተወለደ እንረዳለን፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት ልደታት አሉት፡፡እሱም ከላይ የተመለከትነው ሲሆን ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ኢሳይያስ እንዲህ ሲል መስክሯል፡፡ “ሕፃን ተወልዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶልናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡፡ ስሙም ድንቅ፣ መካር፣ ኃያል አምላክ የዘለዓለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል”(ኢሳ.፱፥፮)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ኢሳይያስ ሕፃን ተወልዶልናል ያለው ድኅረ ዓለም ከድንግል ማርያም መወለዱን ሲያጠይቅ ነው፡፡ ከሦስቱ አካል አንዱ አካል በባሕርዩ  ሲመሰገን   ሲወደስ   የነበረው   በአምላካዊ   ባሕርዩ በመፍጠር፣  በመግዛት፣ በመመለክ፣ በመፍረድ፣ በጌትነት ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከእግዚአብሔር መንፈስ   ቅዱስ ጋር በአንድነት የነበረው፣ ያለው፣ የሚኖረው እርሱ እግዚአብሔር ወልድ ዓለምን ያድን ዘንድ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ መወለዱን  ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ “የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ” ያለው የኢየሱስ ክርስቶስን ከድንግል ማርያም መወለድ መሆኑን በግልጽ የሚያስረዳ ነው፡፡

ይህው ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ “በመጀመሪያ ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ ይህም በመጀመሪያ በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ ሁሉም በእርሱ ሆነ ከሆነውም ሁሉ ያለ እርሱ ምንም የሆነ የለም… ያም ቃል ሥጋ ሆነ በእኛም አደረ ለአባቱ አንድ እንደሆነ ልጅ ክብር ያለ ክብሩን አየን ጸጋንና እውነትን የተመላ ነው”(ዮሐ.፩፥፩-፲፬)፡፡

“የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ” ማለትም አምላክ ሰው ሆነ፤ ሰውም አምላክ ሆነ፤ አካላዊ ቃል ሥጋን በመዋሐዱ (ሰው በመሆኑ) የማይታየው ታየ፣ የማይወሰነው ተወሰነ፣ ረቂቁ ገዝፎ (ጎልቶ) ታየ፣ የማይዳሰሰው ተዳሰሰ ማለት ነው፡፡ ይህ የሆነውም በደኀራዊ ልደቱ ነው፡፡ በደኀራዊ ልደቱ ዓለምን ለማዳን በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በሥጋ በመገለጡ ቀዳማዊ ልደቱ ታውቋል፡፡

የሰው ልጅ ድኅነትን ያገኘው የእግዚአብሔር ልጅ ዳግም በመወለዱ ነው፡፡ የኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ተለያይተው የነበሩትን ሰውና መላእክት አንድ ያደረገ፤ ሕዝብና አሕዛብን አንድ ወገን ያደረገ የእግዚአብሔር የማዳን ሥራ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ መገለጡም የሰው ልጅ በበደሉ ምክንያት በድቅድቅ ጨለማ ተውጦ፣ በሞት ጥላ ሥር ወድቆ፣ ሳለ አማናዊው ብርሃን መታየቱ ሰውን የመውደዱ  ምሥጢር ነው፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ “ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅንም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” (ኢሳ.፯፥፲፬) ያለው   መፈጸሙን ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ደግሞ “እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ይሉታል፡፡ ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው” (ማቴ.፩፥፳፫) ሲል ተርጉሞታል፡፡

ስለዚህ የእግዚአብሔር ልጅ መገለጥ (ሰው መሆን) እግዚአብሔር የሰውን ልጅ በምሕረት መመልከቱ፣ ከጽድቅ ተራቁቶ ለነበረው የጸጋ ልብስ ስለመሆኑ ብርሃን ሆኖ ድቅድቁን ጨለማ ያራቀ መሆኑን የሚያስረዳ ነው፡፡

ለዚህም ቅዱስ ዮሐንስ በመጀመሪያው መልእክቱ “ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል እንመሰክርማለን ከአብ  ዘንድ  የነበረውንም ለእኛም  የተገለጠውን የዘለዓለምን ሕይወት እናወራላችኋለን” (፩ኛዮሐ.፩፥፪) በማለት ምስክርነቱን ገልጾልናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ እንዳለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣበትንና በሥጋ የተገለጠበትን ምክንያት ሲጠቅስም በርእሳችን መነሻ ያደረግነውን የእግዚአብሔር ልጅ የመገለጡን ዓላማ ሲያብራራም፡-

“ኃጢአትን የሚሠራት ሁሉ እርሱ በደልን ደግሞ ያደርጋል ኀጢአት በደል ናትና እርሱም ኀጢአትን ያስወግድ ዘንድ እንደ ተገለጠ ታውቃላችሁ በእርሱም ኀጢአት የለም በእርሱም የሚኖር ሁሉ አይበድልም የሚበድልም ሰው አያየውም አያውቀውምና ልጆቼ ሆይ ማንም አያስታችሁ እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ጽድቅን የሚያደርግ ሁሉ ጻድቅ ነው ኀጢአትን የሚሠራትም ከሰይጣን ወገን ነው ጥንቱን ሰይጣን በድሎአልና ስለዚህ የሰይጣንን ሥራ ይሽር ዘንድ የእግዚአብሔር ልጅ ተገለጠ”(፩ኛዮሐ.፫፥፬-፱)እንዲል፡፡

በአምላክ ሰው መሆን(መወለድ) ከኀጢአት ማሰሪያ፣ከዲያብሎስ ቁራኝነት፣ከሲኦል ባርነት ነጻ ወጥተናል፡፡እግዚአብሔር በፍጹም ፍቅሩ ወደ ራሱ አቀረበን፣አባ አባት ብለን እንጠራው ዘንድ በልጅነት ጸጋ አከበረን፣የሞትን ቀንበር ከላያችን አንከባሎ ጣለልን፣በማዳኑ ሥራ ከጨለማው ገዢ ታደገን፣ወደ ቀድሞ ክብራችንም እንመለስ ዘንድ ከራሱ ጋር አስታረቀን፣እርሱ ከእኛ ጋር ሲሆን ሞት ከፊታችን ተወገደ በዚህ ሁሉ ክብርና ጸጋ የጎበኘን ፍጹም አምላክ ሲሆን ፍጹም ሰው ሆኖ ነውና ክብርና ምስጋና ለእርሱ ለልዑል እግዚአብሔር ይሁን፡፡ በሚቀጥለው ክፍል  የመገለጡን ምሥጢር በስፋት የምንመለከት ይሆናል እስከዚያው ይቆየን፡፡

የጸሎት ጊዜያት

በእንዳለ ደምስስ

ክፍል አምስት

“የጽድቅን ጥሩር ልበሱ” በሚል ርእስ አራት ተከታታይ ክፍሎችን ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው ክፍል አምስት መርሐ ግብራችንም የጸሎት ጊዜያትን እንቃኛለን፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን የጸሎት ጊዜያት የታወቁ ናቸው፡፡ ጸሎትን አስመልክቶ ቅዱሳት መጻሕፍትን መሠረት አድርገን ቤተ ክርስቲያናችን የደነገገቻቸውን ሰባቱን የጸሎት ጊዜያት ከነምክንያታቸው አንደሚከተለው እንመለከታለን፡- ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ስለ እውነት ፍርድህ ሰባት ጊዜ በቀን አመሰግንሃለሁ” እንዲል(መዝ. ፻፲፰.፻፷፬)፡፡

ጸሎተ ነግህ፡-

ፀሐይ ከመውጣቱ በፊት ከእንቅልፋችን ነቅተን ከመኝታችን ተነሥተን በማለዳ የምንጸልው ጸሎት ነው፡፡ ይህም እግዚአብሔር የሌሊቱን ጨለማ አሳልፎ ብርሃኑን አብርቶልናልና ስለዚህ ማለዳ መጸለይ ለክርስቲያን ሁሉ የታዘዘ ነው፡፡ በሰላም አሳድሮ፣ ጨለማውን አሳልፎ ለብርሃን አብቅቶናልና ይህን ላደረገ እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ፣ ቀኑንም በሰላም ያውለን ዘንድ፣ ሥራችንንም ይባርክልን ዘንድ መጸለይ ለክርስቲያን የሚገባ ነው፡፡

መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት “በማለዳ ቃሌን ስማኝ፣ በማለዳ በፊትህ እቆማለሁ፣ እገለጥልሃለሁም” (መዝ.፭.፫) በማለት እንደተናገረው በማለዳ ከእንቅልፋችን ተነሥተን ልንጸልይ ይገባል፡፡

ሌላው በመጽሐፈ አክሲማሮስ እንደተገለጸው እግዚአብሔር አምላካችን አዳምን ከምድር አፈር ያበጀበትና እስትንፋስን ሰጥቶ የፈጠረው ስለሆነ፣ እኛንም ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣንን(የፈጠረንን) አምላካችንን ለማመስገን በማለዳ እንጸልያለን፡፡ (ዘፍ.፩.፳፮)፡፡

የሠለስት(ሦስት) ሰዓት ጸሎት፡-

ጠዋት በሦስት ሰዓት የምንጸልይበት ምክንያት በርካታ ቢሆኑም ጥቂቶቹን እንመለከት፡-

፩. ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤል በባቢሎን በምርኮ በነበረበት ጊዜ ዘወትር መስኮቱን በምሥራቅ አቅጣጫ ከፍቶ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ “የእልፍኙም መስኮቶች ወደ ኢየሩሳሌም አንጻር ተከፍተው ነበር፣ ቀድሞም ያደርግ እንደነበረ ከቀኑ በሦስት ሰዓት በጒልበቱ ተንበርክኮ በአምላኩ ፊት ጸለየ፣ አመሰገነም፡፡”(ዳን.፮.፲)፡፡ እኛም ቅዱሳን አባቶቻችን በሄዱበት መንገድ መጓዝ፣ ሥርዓቱንም መፈጸም ተገቢ ነውና በዚህ ሰዓት ለጸሎት በአምላካችን ፊት እንቆማለን፡፡

፪. ሌላው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በቤተ መቅደስ ሐሩንና ወርቁን አስማምታ ስትፈትል መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ወደ እርስዋ ተልኮ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና እንደምትወልድ ያበሠረበት ሰዓት ነው፡፡ “. . . መልአኩም እንዲህ አላት “ማርያም ሆይ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና አትፍሪ፡፡ እነሆ ትፀንሻለሽ፣ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ ስሙንም ኢየሱስ ትይዋለሽ፣ እርሱም ታላቅ ነው፤ የእግዚአብሔር ልጅም ይባላል” አላት፡፡ (ሉቃ.፩.፳፮)፡፡

፫. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጲላጦስ አደባባይ የተገረፈበትንና ጲላጦስ ለካህናት አለቆችና ጸሓፊዎች፣ ለሸንጎውም ይሰቅሉት ዘንድ አሳልፎ የሰጠበትን በማሰብ ነው፡፡ ያለ በደልህ ስለ እኛ ብለህ ተከሰስህ፣ ተገረፍህ፣ አሳልፈውም ሰጡህ እያልን አምላካችን ስላደረገልን ካሳ እያሰብን እንጸልያለን፡፡ “ስቀለው፣ ስቀለው እያሉ አብዝተው ጮኹ፡፡ ጲላጦስም የሕዝቡን ፈቃድ ሊያደርግ ወድዶ በርባንን ፈታላቸው፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ገርፎ ሊሰቅሉት ሰጣቸው” እንዲል (ማቴ.፳፯.፳፮፤ማር.፲፭.፲፭)፡፡

፬. በሦስት ሰዓት ሐዋርያት በአንድነት ተሰብስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ የወረደላቸው ሰዓት ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤውን ከገለጠበት ጊዜ አንስቶ ሐዋርያት በአንድነት ሆነው እንዲጸልዩ፣ ከኢየሩሳሌምም እንዳይወጡ አስጠንቅቋቸው ዐርባውን ቀን መጽሐፈ ኪዳንን ሲያስተማራቸው ቆይቷል፡፡ በኀምሳኛውም ቀን በዕለተ እሑድ ከጠዋቱ በሦስት ሰዓት ኃይልን ይለብሱ ዘንድ፣ በጥብዓት ሆነው ይህንን ዓለም በወንጌል ያረሰርሱ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ልኮላቸዋል፣ ሰባ ሁለት ቋንቋዎችንም ገልጦላቸው ተናግረዋል፡፡ መንፈሳዊ ኃይልንም ተላብሰዋል፡፡ በዕለቱም በሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ስብከትም ሦስት ሺህ ሰዎች አምነዋል፡፡  መጽሐፍ ቅዱስ ይህንን ሲያብራራ እንዲህ ይላል፡- “ኀምሳውም ቀን በተፈጸመ ጊዜ ሁሉም በአንድነት በአንድ ቦታ ተሰብስበው ነበር፡፡ ድንገትም እንደ ዐውሎ ነፋስ ድምፅ ያለ ከሰማይ ድምፅ መጣ፣ የነበሩበትንም ቤት ሞላው፡፡ እንደ እሳት የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎችም ታዩአቸው፣ በሁሉም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ ሁሉም መንፈስ ቅዱስን ተሞሉ፣ ይናገሩ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እንደ አደላቸው መጠንም እያራሳቸው በሀገሩ ቋንቋ ይናገሩ ጀመሩ” (ሐዋ.፪.፩-፬)፡፡ ስለዚህ እኛም በሓዋርያት ያደረ መንፈስ ቅዱስ ያድርብን ዘንድ በዚህ ሰዓት እንድንጸልይ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡

ስድስት ሰዓት(ቀትር)፡-

ይህ ሰዓት ፀሐይ የሚበረታበትና አጋንንት የሚሠለጥኑበት ሰዓት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት እንዲህ እንደተናገረ “በማታና በጥዋት፣ በቀትርም እናገራለሁ፣ አስረዳለሁ፣ ቃሌንም አይሰሙኝም፣ ከእኔ ጋር ካሉት ይበዛሉና” እንዲል(መዝ.$፬.፲፯-፲፰፤መዝ.፺.፮)፡፡ ስለዚህ ለአጋንንት እንዳንንበረከክና እንዳንሸነፍ ተግተን የምንጸልይበት ሰዓት ነው፡፡

በቀትር ዲያብሎስ አባታችን አዳምን ያሳተበት ስዓት ስለሆነም በጸሎት ድል እንነሣው ዘንድ የምንበበረታበት ሰዓት ነው፡፡

እንዲሁም አይሁድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከቀኑ ስድስት ሰዓት የሰቀሉበት ጊዜ ነው፡፡ ከስድስት ሰዓት እስከ ዘጠኝ ሰዓትም ሰባት ተአምራት ተደርገዋል፡፡ በሰማይ ፀሐይ ጨለመ፣ ጨረቃ ደም ለበሰች፣ ከዋክብት ረገፉ፣ በምድር ደግሞ መቃብራት ተከፈቱ፣ ሙታን ተነሡ፣ ዓለቶች ተሰነጠቁ፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃ ለሁለት ተቀደደ፡፡ “ከዚህም በኋላ ሊሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው፣ ጌታችን ኢየሱስንም ተቀብለው ወሰዱት፡፡ መስቀሉንም ተሸክሞ በዕብራይስጥ ጎልጎታ. ወደተባለው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ወጣ፡፡ በዚያም ሰቀሉት” እንዲል(ዮሐ.፲9.፲፬)፡፡ እኛም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ሲል መገረፉን፣ መስቀል ተሸክሞ መውደቅ መነሣቱን፣ መራብ መጠማቱን፣ እንዲሁም መሰቀሉን እያሰብን በስድስት ሰዓት እንጸልያለን፡፡

ዘጠኝ ሰዓት፡-

ቅዱሳን መላእክት ለአገልግሎት የሚፋጠኑበት፣ የሰው ልጆች የሚያቀርቡትን ልመና እና  ጸሎት፣ ዕጣን ወደ እግዚአብሔር የሚያሳርጉበት ሰዓት ነው፡፡ “ሌላ መልአክም መጣ፣ በመሰዊያው ፊትም ቆመ፣ የወርቅ ጥናም ይዞ ነበር፤ በዙፋኑ ፊት ባለው በወርቁ መሰዊያም ላይ ለቅዱሳን ሁሉ ጸሎት እንዲያሳርገው ብዙ ዕጣን ተሰጠው፡፡ የዕጣኑ ጢስም ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡  (ራዕ.፲.፫)፡፡

ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ዮሐንስ ዘወትር ለጸሎት ወደ ቤተ መቅደስ ይገቡበት የነበረ ሰዓት ነው፡፡ በዚያም ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ ሽባ የነበረውን ሰው ፈውሰዋል፡፡ (ሐዋ.፫.፩)፡፡

የመቶ አለቃው ቆርኔሌዎስ በዘጠኝ ሰዓት ጸሎት ያቀርብበት የነበረ ሰዓት ነው፡፡ “በቂሳርያ ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበር ኢጣሊቄ ለሚሉት ጭፍራም የመቶ አለቃ ነበር፡፡ እርሱም  ጻድቅና ከነቤተሰቡ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነበር፣ ለሕዝቡም ብዙ ምጽዋት ይሰጥ ነበር፣ ዘወትርም ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክም በራእይ ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት በግልጥ ታየው”(ሐዋ.፲.፩-፴፪) እንዲል፡፡

በተጨማሪም የጻድቅ ሰው ጸሎት ወደ እግዚአብሔር እንደሚደርስና ዋጋ እንደሚያሰጥ ሲነግረን “የዛሬ አራት ቀን በዘጠኝ ሰዓት በቤቴ ስጸልይ ፊቱ የሚያንጸባርቅ ልብስ የለበሰ አንድ ሰው በፌቴ ቆሞ ታየኝ፡፡ እንዲህም አለኝ፡- ቆርኔሌዎስ ሆይ በእግዚአብሔር ፊት ጸሎትህ ተሰማ፣ ምጽዋትህም ታሰበልህ” እያለ ተገልጾለታል፡፡(ሐዋ.፲.፴-፴፩)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ሲል ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው የለየበት ሰዓትም በመሆኑ ይህንን እያሰብን በዚህ ሰዓት እንጸልያለን፡፡ (ማቴ.፳፯.#5-$፤ማር.፲5.፴፫-፴፬)፡፡

ሠርክ(አሥራ አንድ ሰዓት)፡-

ሰው ቀኑን ሙሉ ሲለፋ ሲደክም ውሎ በሠርክ የሠራበትን ዋጋ የሚቀበልበት ሰዓት ነው፡፡ በመልካምም ሆነ በክፉ ሥራችን ክፍያ እናገኛለን፡፡ በምግባር በሃይማኖት ጸንተን አንደበታችንን ከክፉ ነገር፣ ዐይናችንን ክፉ ከማየት ከልክለን፣ ምግባር ሃይማኖት ይዘን ለሌሎች መልካም በማድረግ፣ ለሀገር ለወገን የሚጠቅም ሥራ ሠርተን ከተገኘን፣ የበደልነውን ክሰን፣ በንስሓ ታጥበን በሃይማኖት ከጸናን “ኑ የአባቴ ቡሩካን” ተብለው ከሚጠሩት ወገን እንደመራለን፡፡ ቀን ክፉ ብንሠራ፣ ሌሎችን እየበደልንና እያስለቀስን፣ እየዋሸንና እየቀጠፍን ከዋልን እንዲሁ “አላውቃችሁም” ከሚባሉት እንቆጠራለን፡፡ ስለዚህ ሰሎሞን በምሳሌው “ልብህ በኃጠአተኞች አይቅና፣ ነገር ግን ቀኑን ሙሉ እግዚአብሔርን በመፍራት ኑር” እንዳለው እግዚአብሔርን በመፍራት መኖር ለሰው ሁሉ የሚገባ ነው፡፡

ከሥራ በኋላ የሠሩበትን ዋጋ መቀበል እንደሚያስፈልግ ሁሉ የእግዚአብሔር ቸርነት ታክሎበት በመጨረሻው ዘመንም ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዋጋችንን እንቀበላለን፡፡  የክርስቲያን ዋጋው መንግሥተ ሰማያት ናት፡፡ (ማቴ.፳.፩-፲6)፡፡

ቅዱስ ዳዊት “ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ፣ እጆቼ የሠርክ መሥዋዕትን አነሡ” በማለት እንደተናገረው በዚህ ሰዓት ጸሎት መጸለይ እንደሚገባ ቀደምት አባቶቻችንን ምሳሌ አድርገን መትጋት ከክርስቲያኖች የሚጠበቅ ነው፡፡(፻#.፪)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ያቀረበው መሥዋዕት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነትን ያገኘበት ሰዓት ነው፡፡ ነቢዩ ለሦስት ዓመት ተኵል ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን ከለጎመ በኋላ የአክአብን ሐሰተኞች ነቢያት በጸሎቱ ድል የነሣበትና እግዚአብሔር መሥዋዕታቸውን የተጠየፈበት ነገር ግን ኤልያስ ያቀረበውን ጸሎትና መሥዋዕት የተቀበለበት ሰዓት ነው፡፡ (፩ነገ.፲፰.፴፮-#)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ መቃብር መውረዱን የምናስብበት ሰዓት ነው፡፡ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የጌታችንን ሥጋ ከመስቀል ላይ አውርደው በአዲስ መቃብር የቀበሩበትም ሰዓት ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ሰዓት በኃጢአት ምክንያት የሞት ሞት የሞትነውን እኛን ለማዳን ሲል ወደ መቃብር መውረዱን እያሰብን እንድንጸልይ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት ሠርታልናለች፡፡(ማቴ.፳፯.$፯-%6፤ ማር.፲5.ማር.#፪-#፯፤ ሉቃ.፳፬.$-$5)፡፡

ንዋም(የመኝታ ሰዓት)፡-

የሰው ልጆች በአዳም በደል ምክንያት ከእግዚአብሔር የተፈረደብንን ፍርድ ለመፈጸም በወዛችንና በላባችን፣ ወጥተን ወርደን እንበላ ዘንድ እንደክማለን፡፡ “…እሾህና አሜኬላን ታበቅልብሃለች፣ የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡ ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራህን ትበላለህ” እንዲል፡፡(ዘፍ.፫.፲፰)፡፡

ቀኑን ሙሉም ስንሠራ ስንለፋ ውለን ማታ እናርፋለን፡፡ በማረፊያችን ሰዓት ደግሞ ኦርቶዶክሳውያን በሌሎቹ ሰዓታት እንደምንጸልይ ሁሉ ወደ መኝታ ከመሄዳችን በፊት መጸለይ ተገቢ ነው፡፡ በሰላም ያዋልከን አምላካችን ሆይ እናመሰግንሃለን፣ ቀኑን በሰላም አሳልፈህልናልና ሌሊቱንም ባርከህ ቀድሰህ ታሳድረን ዘንድ ቅዱስ ፈቃድህ ይሁን እያልን ወደ መኝታ ከመሄዳችን በፊት አምላካችንን እያመስገንን፣ በደላችንንም ይቅር በለን እያልን እንጸልያለን፡፡

እንዲሁም ይህ ሰዓት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በጌቴሴማኒ ሥርዓተ ጸሎት ያስተማረበት ሰዓት ነው፡፡ (ማቴ.፳፮.፴፮)፡፡

መንፈቀ ሌሊት፡-

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በግርግም፣ በከብቶች በረት የተወለደበትን ሰዓት እያሰብን በዚህ ሰዓት እንጸልያለን፡፡ (ማቴ.፪.፩-፲፡ ሉቃ.፪.6-፲፫)፡፡ እንዲሁም በመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ የተጠመቀበት ሰዓት ስለሆነ ይህንን እያሰብን እንጸልያለን፡፡(ማቴ.፫.፲፫፤ሉቃ.፫.፳፩፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ የተነሣበትና በዕለተ ምጽአትም ጊዜው ሲደርስ ይህንን ዓለም ያሳልፍ ዘንድ በግርማ መለኮት በክበበ ትስብእት ሠራዊተ መላእክትን አስከትሎ የሚመጣበት ሰዓት ስለሆነ በትጋት እንጸለይ ዘንድ ታዘናል፡፡(ማቴ.፳5.6፤ዮሐ.፳.፩፤ማር.፲፫.፴፭)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “አመሰግንህ ዘንድ በእኩለ ሌሊት እነሣለሁ”(መዝ.፻፲፰.፷፪) ብሎ እንደተናገረ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ምጽአት ይህንን ዓለም ለማሳለፍ በመንፈቀ ሌሊት እንደሚመጣ እያሰብን የምንጸልበት ጊዜ ነው፡፡

ጳውሎስና ሲላስም በእስር ቤት እያሉ በዚህ ሰዓት ወደ እግዚአብሔር ይጸልዩ ነበር፡፡ “በመንፈቀ ሌሊትም ጳውሎስና ሲላስ ጸለዩ፡፡ እግዚአብሔርንም በዜማ አመሰገኑት፡፡” በማለት ቅዱስ ሉቃስ እንደገለጸው እኛም በመንፈቀ ሌሊት ልናመሰግን ይገባል፡፡(ሐዋ.፲6.፳፭)፡፡

የሰባቱ የጸሎት ጊዜያት ብዙ ምክንያት ቢኖራቸውም በአጭሩ እነዚህን ከላይ የጠቀስናቸውን በማሰብ እንጸልያለን፡፡

እግዚአብሔር ቢፈቅድ በክፍል ስድስት ዝግጅታችን ስግደትን እንመለከታለን፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡ አሜን፡፡

ይቆየን፡፡

አዳም አርብ ቀን ተፈጠረ (ዘፍ.፩፥፳፯)

መ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

አዳም ማለት፡- ያማረ መልከ መልካም ውብ ፍጡር ማለት ነው፡፡ አዳም የተፈጠረው ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ እና ከሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ ነው፡፡ አራቱ ባሕርያተ ሥጋ የሚባሉት ውኃ፣ እሳት፣ ነፋስ፣ መሬት ሲሆኑ ሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ የሚባሉት ደግሞ ለባዊት(የምታስብ)፣ ነባቢት(የምትናገር)፣ ሕያዊት(የምትኖር) ወይም በሌላ አገላለጽ ልብ፣ ቃል፣ እስትንፋስ ማለት ነው፡፡

እግዚአብሔር  አምላክ  እሑድ  ፍጥረትን  መፍጠር  የጀመረባት  ቀን  ናት፡፡  ለዚህም  ነው በሥነ ፍጥረት ታሪክ እሑድ የመጀመሪያ ቀን ተብላ የምትጠቀሰው፡፡ የዕለቱ ስያሜም አሐደ፣ አንድ አደረገ ከሚለው የግእዝ ግስ እሑድ የሚለው ቃል የወጣል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ እሑድ ቀን ፍጥረትን መፍጠር አሰበ ሊፈጥር ያሰበውንም እሑድ መፍጠር ጀመረ፡፡ አዳምንም በመጨረሻዋ የሥራ ዕለት በዕለተ ዐርብ በነግህ ከኅቱም ምድር ሚያዝያ አራት ቀን የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ አድርጎ እግዚአብሔር በአርአያውና በአምሳሉ ፈጠረው፡፡ አዳም የተፈጠረውም በምድር መካከል በምትገኘው ኤልዳ እየተባለች በምትጠራ ስፍራ ነው (ኩፋ.፭.፮)፡፡

“እግዚአብሔርም አለ ሰውን በአርአያችንና በአምሳላችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሣዎችንና የምድር አራዊትን የሰማይ ወፎችን እንስሳትን እና ምድርን ሁሉ በምድርም ላይ የሚንቀሳቀሱትን ሁሉ ይግዛ፤ እግዚአብሔርም ሰውን በእግዚአብሔር አምሳል ፈጠረው፤ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው፡፡ …እግዚአብሔርም የፈጠረውን ሁሉ እጅግ መልካም እንደሆነ አየ፤ ማታም ሆነ ጥዋትም ሆነ ስድስተኛም ቀን ሆነ፡፡”(ዘፍ.፩፥፳፮-ፍ)

እግዚአብሔር ፍጥረትን ሁሉ ፈጥሮ ከጨረሰ በኋላ ነው አዳምን በዕለተ ዐርብ የፈጠረው፡፡ ይህም እግዚአብሔር አምላካችን “ቸር አምላክ” ስለ ሆነ ነው፡፡ በጎ አባት ለልጁ የሚበላውን፣ የሚጠጣውን፣ የሚኖርበትን፣ የሚገዛውን፣ የሚመራውን፣ የሚያርስበትን ጥማድ፣ የሚያርሰውን መሬት፣ ወ.ዘ.ተ እንደሚያዘጋጅ ሁሉ ቸር የሆነው አምላካችንም ሁሉን ከፈጠረና ካዘጋጀለት በኋላ ሁሉን ወራሽ ሊያደርገው በዕለተ ዐርብ አዳምን አክብሮና አልቆ በአርአያውና በአምሳ ፈጠረው፡፡ በአዘጋጀለት በከበረ ስፍራም የፈጠረለትን ሁሉ እንዲገዛ በሁሉ ላይ አሠለጠነው፡፡

እንዲሁም አንድ ሰው ድግሥ ደግሦ ታላቅ የሚለውን ሰው ሲጠራ በክብር የተጠራው ታላቅ እንግዳ ከመምጣቱ አስቀድሞ ቤቱን ጎዝጉዞ፣ ሰንጋውን ጥሎ፣ እንጀራውን፣ ወጡን አሰናድቶ እንዲጠብቅ እና ያ በክብር የተጠራ ታላቅ እንግዳ በተዘጋጀበት መጥቶ ደስታውን እንዲካፈል አዳምም በእግዚአብሔር የተወደደ፣ የከበረ ታላቅ እንግዳ ፍጡር ሆኖ ፍጥረት ሁሉ ተፈጥረው በተጠናቀቁበት ሊገዛቸው፣ ሊነዳቸውና ሊኖርባቸው፣  ሊሠለጥንባቸውም በመጨረሻ ተፈጠረ፡፡

አባታችን አዳም በዕለተ ዐርብ ሲፈጠር  እንደ መላእክት ንጹሕ ነበር፡፡ በዚህ ንጽሕናውም ረዳት ሆና ከጎኑ ከተፈጠረችለት ሔዋን ጋር በገነት ለሰባት ዓመት ያህል ኖረ፡፡ ከዚህ በኋላ ግን በዲያብሎስ አሳችነት ምክንያት ወደ ምድረ ፋይድ ተሰደደ፡፡ ከገነት ተሰዶም ለመመለስ የፈጀበት ጊዜ ከነ ልጅ ልጆቹ አምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመት ነው፡፡ ይህም እግዚአብሔር የሰጠው የተስፋ ቃል እስኪፈጸም ማለት ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የዘመኑ ፍጻሜ ሲደርስ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ እንዳለው ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ አዳምን ቀድሞ በፈጠረበት ዕለት በዕለተ ዐርብ በመልዕልተ መስቀል ተሰቅሎ በደሙ ፈሳሽነት ሰውን ከበደል ሁሉ አነጻው፡፡ ወደ ቀደመ ክብሩም መለሰው፡፡ አዳምና የልጅ ልጆቹ በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ገነትን ሊወርሱ ችለዋል፡፡

አዳም በዕለተ ዐርብ ተፈጥሮ በበደል ምክንያት ያጣትን ገነት በዕለተ ዐርብ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል መሞት ዳግም ሊወርሳት ችሏል፡፡ ስለዚህ ዕለተ ዐርብ የተፈጠርንባትም፣ የዳንባትም ዕለት ናትና ዕለቲቱን በጾም በጸሎት አስበናት እንውላለን፡፡ ከዚሁ በተያያዘም ዕለተ ረቡዕም እንዲሁ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሞት በአይሁድ ዘንድ ተመክሮ የዋለበት ነው፡፡

ረቡዕ ምክረ አይሁድ፣ ዐርብ ስቅለተ ክርስቶስ የተፈጸመበት ቀን ስለ ሆነ ዐርብ እና ረቡዕ በኦርቶዶክሳውያን ዘንድ በጾም ታስበው ይውላሉ፡፡ ወሩ የፍስክ ጊዜ ቢሆን እንኳ ከበዓለ ኀምሣ ውጪ ዐርብ እና ረቡዕ በጾም ሁል ጊዜ ይታሰባሉ፡፡ ልደትና ጥምቀት ዐርብ ወይም ረቡዕ ላይ በዋሉ ጊዜ ተለዋጭ ቀን ጾመ ገሃድ ተብሎ በዋዜማቸው ይጾማል፡፡ ይህም ከበዓሉ ታላቅነት የተነሣ በደስታ በዓላቱ እንዲከበሩ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሠራችው ሥርዓት መሠረት ነው፡፡

ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዐርብና ረቡዕ በክርስቲያኖች ዘንድ ከሌሎች ቀናት ተለይተው ቅዳሴውም ከሰዓት እንዲቀደስ እና በእነዚህ ዕለታት አራስ ከሆነች እናት፣ ከሰባት ዓመት ዕድሜ በታች ካሉ  ከሕፃናት እና ሕመም ከጸናበት ሰው በቀር ሁላችንም መጾም እንዳለብን የምታስተምረን፡፡ ይህ ሁሉ እግዚአብሔር ለሰው ያሳየውን ታላቅ ፍቅር የምናይበትና የምናስተውልበት  ስለሆነ ምስጋና ይድረሰው አሜን፡፡

እንዴት እንጸልይ?

ክፍል ፬

በእንዳለ ደምስስ

ባለፈው ዝግጅታችን “የጽድቅን ጥሩር ልበሱ” በሚል ርእስ ክፍል ሦስትን ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው ዝግጅት ደግሞ ቀጣዩን ክፍል ፬ ወደ ድረ ገጻችን ተከታታዮች የምናቀርብ ይሆናል፣ ተከታተሉን፡፡

ጸሎት መለመን፣ ማመስገን፣ በንጽሕና በእግዚአብሔር ፊት መቆም፣ ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር ስንነጋገር ደግሞ ልናደርጋቸው የሚገቡ ጥንቃቄዎችና ይዘን መገኘት የሚገቡን መንፈሳዊ ምግባራትን ማወቅና መረዳት፣ በአጠቃላይ እንዴት መጸለይ እንዳለብን ጠንቅቀን መገንዘብ ይኖርብናል፡፡ እንኳን ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት ለመነጋገር ቀርቶ ከማንኛውም ሰው ጋር ከመነጋገራችን በፊት ምን ማለት እንዳለብን፣ በምን ጉዳይ ላይ እንደምንነጋገር ለይተን ማወቅን ይጠይቃል፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔርን በጸሎት ለመጠየቅና ለመነጋገር ስናስብ ዝግጅት ማድረግ እንደሚገባን ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ በሃይማኖት ቆመን፣ ሰማያዊውን ነገር እያሰብን ለጸሎት መዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡

በዚህም መሠረት  ልናከናውናቸውና ይዘን መገኘት የሚገቡን መንፈሳዊ ምግባራት ምን ምን እንደሆኑ ማየት ያስፈልጋል፡፡ በወንጌል አምስቱ ልባም ሴቶች ያደረጉትንም ማስተዋል ይገባል፡፡ “ያን ጊዜም መንግሥተ ሰማያት መብራታቸውን ይዘው ሙሽራውን ለመቀበል የወጡ ዐሥሩን ደናግል ትመስላለች፡፡ ከእነርሱም ውስጥ አምስቱ ሰነፎች፣ አምስቱም ልባሞች ነበሩ፡፡ ሰነፎቹ መብራታቸውን ይዘው ዘይት አልያዙም ነበር፡፡ ልባሞቹ ግን ከመብራታቸው ጋር በማሰሮዎቻቸው ዘይት ይዘው ነበር” እንዲል(ማቴ.፳፭.፫)፡፡ ሃይማኖት፣ ጾም፣ ጸሎት፣ ትሕትናና ፍቅር መያዛቸውን ሲያመለክት አምስቱን ልባሞች አላቸው፡፡ ስለዚህ ከመጸለያችን በፊት እነዚህን ይዘን በመገኘት ከዚህ በታች ለተዘረዘሩት ነጥቦች ትኩረት ልንሰጥ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህም፡-

፩. ኀጢአተኛ መሆናችንን ማሰብ፡-

ጢአት በኀልዮ(በማሰብ፣ በነቢብ(በመናገር)፣ በገቢር(በማድረግ) ሊፈጸም ይችላል፡፡ ያደረግነው ጥፋት ትክክል እንዳልበር፣ በሠራነው ኀጢአትም እግዚአብሔርን፣ ሌሎችን ሰዎች፣ እንዲሁም ራሳችንን መጉዳታችንን ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ራሳችንን እንዴት እንጎዳለን ስንል እግዚአብሔር በአርአያውና በምሳሌው ፈጥሮን፣ በሠራልን ሕግና ሥርዓት እንጓዝ ዘንድ ሲገባን ቃሉን አፍርሰናልና ሥጋችንን እናረክሳለን፡፡ ፈሪሳውያን አንዲት ሴትን ዝሙት ስትፈጽም አግኝተናታል ብለው በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ አቅርበዋት ነበር፡፡ ኀጢአት ስትሠራ አግኝተናታልና በሙሴ ሕግ መሠረት በድንጋይ ተወግራ እንድትሞት አስበው፣ እንዲሁም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመፈተን ይህንን አድርገዋል፡፡ የራሳቸውን ኃጢአት ዘንግተው የሌላውን ኃጢአት ለመመልከት ፈጥነዋል፡፡ ነገር ግን የጌታችን መልስ እንደጠበቁት አልነበረም፡፡ ሊፈትኑት ቀርበዋልና ልብንና ኵላሊትን የሚመረምር አምላክ ነውና “ከእናንተ ኃጢአት የሌለበት አስቀድሞ ድንጋይ ይጣልባት” አላቸው፡፡ እነርሱም ኅሊናቸው ወቀሳቸው፡፡ “ከሽማግሌዎች እስከ ኋላኞቹ ድረስ አንዳንድ እያሉ ወጡ” እያለ ይነግረናል፡፡ ቀድሞ ከሌሎች ይልቅ የራስን ኃጢአት ማሰብ፣ ንስሓም መግባት ሲገባቸው የሌሎችን ኃጢአት ለመቁጠር ልባቸውን አስጨክነው ቀረቡ፡፡ ነገር ግን ያልጠበቁት ጥያቄ ሲቀርብላቸው ወደ ራሳቸው ኀጢአት ተመለከቱ፣ እንደበደሉም አወቁ፡፡(ዮሐ.፰.፯-9)፡፡

በደላችንን ማሰብ ከእያንዳንዳችን የሚጠበቅ ነው፡፡ ስለዚህ ለጸሎት ከመቆማችን በፊት እኛ በእግዚአብሔር ፊት መቆም የማንችልና የማይገባን እንደሆንን ማሰብና መረዳት ያስፈልጋል፡፡ በእግዚአብሔር ፊት በእኛ ሥልጣንና ፍላጎት ሳይሆን በእግዚአብሔር ቸርነት በተሰበረ ልብ መቆማችንን ልናስተውል፣ ይህንንም አምነን ተቀብለን ተግባራዊ ልናደርግ ግድ ይለናል፡፡ አይሁድ ከጌታችን ጋር እርሱ ወደሚሄድበት መሄድ እንደማይችሉ ከነገራቸው በኋላ “እኔ እሄዳለሁ፣ ትሹኛላችሁም፣ ነገር ግን አታገኙኝም በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁ” ብሏቸዋል፡፡ ኃጢአት ወደ ሞት እንደሚወስድ አመልክቷቸዋል፤ ኃጢአተኞች ሆነው ሳለም በትዕቢት ልባቸውን በማደንደን ተፈታትነውታልና ገሰጿቸዋል፡፡(ዮሐ.፰.፳፩)፡፡

አይሁድ የአብርሃም ዘሮች ነን እያሉም ይመኩ ስለነበር ራሳቸውን ጻድቅ አድርገው የመቁጠር፣ ከፍ ከፍ ማለትንም መውደድ የተጠናወታቸው በመሆናቸው እንደ ቃሉ መኖር ሲገባቸው ጌታችንን ተፈታትነውታል፡፡ ጌታችንም የልቡናቸውን መደንደን ተመልክቶ “እውነት እውነት እላችኋለሁ ኃጢአትን የሚሠራ ሁሉ የኃጢአት ባሪያ ነው፡፡ ባሪያ ዘወትር በቤት አይኖርም፣ ልጅ ግን ለዘለዓለም ይኖራል” ሲል ከኃጢአታቸው ተመልሰው የእግዚአብሔር ልጆች ይባሉ ዘንድ፣ እንደ ልጅም በቤቱ ይኖሩ ዘንድ ነግሯቸዋል፡፡

“ኃጢአትን የሚሠራት ሁሉ እርሱ በደልን ደግሞ ያደርጋል፣ ኃጢአት በደል ናትና”(፩ኛዮሐ.፫.፬) እንዲል እኛም በደለኞች መሆናችንን እያሰብን፣ በደላችንንም ይቅር ይለን ዘንድ ለጸሎት መቆም ይገባናል፡፡

፪. የበደሉንን ይቅር ለማለት የተዘጋጀ ልብ፡-

አንድ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር የሚፈልገው ነገር እንዳለ ሁሉ እግዚአብሔርም ከሰው ልጆች የሚፈልጋቸው ነገሮች አሉት፡፡ እነርሱም ዐሥርቱ ትእዛዛትና ስድስቱ ቃላተ ወንጌልን መፈጸም ናቸው፡፡ እነዚህም በአንድ መሠረታዊ ትእዛዝ ይጠቃለላሉ፡- ይህም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች በላከው መልእክቱ “ወንድምህን እንደ ራስህ ውደድ፤ የሚለው ቃል ሕግን ሁሉ  ይፈጽማልና፡፡” እንዲል(ገላ.፭.፲፬)፡፡ ወንድማችንን በመውደድ ቢበድለን እንኳን በይቅርታ በማለፍ ይቅር ባይነትን ለሌሎች ማስተማር ያስፈልጋል፤ ለነፍስም ዕረፍትን ይሰጣልና፡፡ የበደልነው ሰው ይቅር እንዲለን የምንሻ ከሆነ እኛም የበደሉንን ይቅር ለማለት የፈጠንን መሆን ይገባናል፡፡ “በምትጸልዩበትም ጊዜ በሰማያት ያለው አባታችሁ በደላችሁን ይቅር እንዲላችሁ በወንድማችሁ ያለውን በደል ይቅር በሉ፡፡ እናንተ ይቅር ባትሉ በሰማያት ያለው አባታችሁም በደላችሁን ይቅር አይላችሁም” እንዲል፡፡(ማር.፲፩.፳፭)፡፡

ልባችንን በግብዝነትና በእልከኝነት ማሠቃየት የለብንም፡፡ በዘወትር ጸሎታችን ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን አባታችን ሆይ ብለን ዘወትር ስሙን እንጠራ ዘንድ ካዘዘን ትእዛዛት ውስጥ “. . . በደላችንን ይቅር በለን፣ እኛም የበደሉንን ይቅር እንል ዘንድ” እያልን እንጸልያለን፡፡ ይህንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አይሁድ በመስቀል ላይ በሰቀሉት ጊዜ ከተናገራቸው “ሰባቱ አጽርሐ መስቀል” መካከል “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” እንዳለ እኛም ለጸሎት ስንዘጋጅ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስን አብነት አድርገን ሌሎች ይቅር እንዲሉን እኛም ይቅር ለማለት የፈጠንን መሆን አለብን፡፡ ልባችንንም ለዚህ ማዘጋጀት ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቅ መሆኑን ከአምላካችን ተምረናልና፡፡

፫. ትሕትና፡-

አንድ ክርስቲያን በክርስቲያንነቱ ሊያሟላቸው ከሚገቡ መልካም ምግባራት መካከል ትሕትና እጅግ አስፈላጊ ከሆኑት ውስጥ ይጠቀሳል፡፡ “ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ፣ ከእኔም ተማሩ፣ እኔ የዋህ ነኝና ልቤም ትሑት ነውና ለነፍሳችሁም ዕረፍትን ታገኛላችሁ፣ ቀንበሬ ልዝብ፣ ሸክሜም ቀላል ነውና” (ማቴ.፲፩.፳9) በማለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን እኛም ትሑታን ሆነን መገኘት ይገባናል፡፡

አምላካችን በሸላቾቹ ፊት እንደሚቆም በግ በትሕትና ቆሟልና እኛም ትሕትናን ገንዘብ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ ትሕትና ዲያብሎስን ድል ማድረጊያ መንፈሳዊ መሣሪያችን ነው፡፡ በትዕቢት የሚመጣውን በትሕትና ማሸነፍ ስለሚቻል፡፡ ለዚህም ቅዳሳን፣ ፃድቃን ሰማዕታት አምላካችንን አብነት እንዳደረጉ ሁሉ እኛም እነርሱ በተጓዙበት መንገድ ልንከተላቸው ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ጸሎት እንዴት መጸለይ አለብን ስንል በእግዚአብሔር ፊት ስንቆም በፍጹም ትሕትና ሊሆን ግድ ይላል፡፡ በትሕትና የምንጸልየው ጸሎት ቅድመ እግዚአብሔር እንደሚደርስም ማመን ከእኛ ይጠበቃል፡፡

፬. አለባበስን ማስተካከል፡-

ለጸሎት በእግዚአብሔር ፊት ለመጸለይ በምንቆምበት ወቅት ልናደርጋቸው ከሚገቡን ነገሮች ሌላው ጉዳይ አለባበስን በተገቢውና ክርስቲያናዊ ሥርዓትን በተከተለ ሁኔታ መልበስ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ስንቆም ነጠላችንን መስቀልያ አጣፍተን መልበስ ስንል ነጠላውን በቅድሚያ ከቀኝ ወደ ግራ፣ እንዲሁም ከግራ ወደ ቀኝ ማጣፋት ይገባል፡፡ ይህም ከቀኝ ወደ ግራ ማጣፋታችን አዳም አባታችን በበደሉ ምክንያት ከገነት ወጥቶ እንደነበር ሲያመለክተን፣ ከግራ ወደ ቀኝ ማጣፋታችንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች በመስቀል ላይ ተሰቅሎ፣ ሞቶ፣ ወደ መቃብር መውረዱን፣ መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል ሞትን ድል አድርጎ መነሣቱንና ዲያብሎስን አሥሮ፣ አዳምንና ልጆቹን ከሲኦል በማውጣት ወደ ገነት መመለሱን ሲያመለክተን ነው፡፡ ስለዚህ ለጸሎት በምንቆምበት ጊዜ ነጠላችንን መስቀለኛ አጣፍተን በተመስጦ ኅሊናችንን በመሰብሰብ፣ ለጸሎት በሁለት እግራችን ቀጥ ብለን በመቆም ልንዘጋጅ ይገባል፡፡

፭. የምንጸልየውን ማወቅ፡-

ለጸሎት ከመቆማችን በፊት ስለምንጸልየው ጉዳይ ማወቅና መረዳትም ያስፈልጋል፡፡ አንድ ክርስቲያን ዘወትር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በደነገገችው ሥርዓት መሠረት የጸሎት ሰዓት ወስኖ መጸለይ እንደሚገባው የታወቀ ነው፡፡ ከጸሎት ተለይቶ ጽድቅ የለምና፡፡ ጸሎት የማይጸልይ ሰው በየቀኑ በውኃ እጦት እየጠወለገ እንደሚሄድ ዛፍ ነው፡፡ ለመጸለይ ደግሞ የምንጸልየውን ማወቅ አስፈላጊ ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን ለምንድነው በእግዚአብሔር ፊት ለመቆም የፈለግሁት ብሎ ራሱን መጠየቅ፣ ለጥያቄውም ራሱ ምላሹን መስጠት አለበት፡፡

የምንጸልየውን ካወቅን እንዲደረግልን የምንፈልገው ላይ ብቻ ትኩረት ማድረግ ሳይሆን እስከ ዛሬ ውጣ ውረዱን አሳልፎ እዚህ ላደረሰን፣ እንዲሁም እንደበደላችን ሳይሆን በቸርነቱ ታድጎን ስላደረገልን መልካም ነገር ምስጋና ማቅረብን መዘንጋት የለብንም፡፡ ስለ ራሳችን ብቻም ሳይሆን ስለ ሀገር፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን፣ ስለታመሙትና ስለ ተሰደዱት፣ . . . ሁሉ መጸለይ ተገቢ ነው፡፡

በተቃራኒው የምንጸልየውን አለማወቅ ከተግሣጽ አያድነንም፡፡ የዘብዴዎስ ልጆች እናት ማርያም ባውፍልያ ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልጆቿን ያዕቆብና ዮሐንስን ይዛ በመቅረብ  “. . . እነዚህ ሁለቱ ልጆቼ በመንግሥትህ አንዱ በቀኝህ፣ አንዱም በግራህ እንዲቀመጡ አድርግልኝ” አለችው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “የምትለምኑትን አታውቁም፣ እኔ የምጠጣውን ጽዋ መጠጣት ትችላላችሁን? እኔስ የምጠመቀውን ጥምቀት ትጠመቃላችሁን?” ሲል ገሥጿቸዋል፡፡  እናታቸው የለመነችው ልመና ምድራዊ ንጉሥ መስሏት ምድራዊውን ሥልጣን ይሰጣቸው ዘንድ ጠየቀች፡፡ ነገር ግን በዕለተ ዐርብ በመስቀል ላይ በተሰቀለ ጊዜ በቀኝና በግራ ይሰቀሉ ብላ የመለመኗን ምሥጢር አልተረዳችም፡፡ ይህንን ሥጢር ባለመረዳትም ለልጆቿ ሕይወትን ሳይሆን ሞትን ለመነች፡፡ ይህም ለእኛ የማይገባና ያልተረዳነውን ልመና ወደ እግዚአብሔር ማቅረብ እንደሌለብን የሚያስተምረን ነው፡፡

፭. እንደ አቅማችን መጸለይ፡-

በመንፈሳዊ ሕይወታችን ውስጥ ልናየው ከሚገባን ነገር አንዱ ለመጸለይ ያለንን አቅም ነው፡፡ በእርግጥ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በእኩል መንፈሳዊ ብቃት ላይ ይገኛል ማለት አይቻልም፡፡ ከማይጸልዩ ክርስቲያኖች አንስቶ ግርማ ሌሊቱን፣ ጸብአ አጋንንቱን፣ ድምጸ አራዊቱን ታግሰው ጤዛ ልሰው፣ ድንጋይ ተንተርሰው፣ ቅጠል በጥሰው ወደ እግዚአብሔር ያለማቋረጥ እስከ ሚጸልዩት አባቶች ድረስ የተለያየ መንፈሳዊ ብቃትና ጸጋ ይኖራል፡፡ ስለዚህ ጸሎት ባለን መንፈሳዊ አቅም ይወሰናል፡፡

ገና ወጣኒ ሆኖ ይህንንም፣ ያንንም ሁሉንምየጸሎት መጽሐፍ ካላጸለይኩ ማለት ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል፡፡ ቀስ በቀስ ማደግ ሲገባ በስሜታዊነት የተጀመረ በመሆኑ እየቀነሱ፣ እየተሰላቹ በመምጣት ጨርሶ ጸሎትን እስከማቋረጥ ሊያደርስ ይችላልና፡፡ በሃይማኖት ጽናት የሚጸለይ ጸሎት እንደ ዛፍ ነው፡፡ ቀስ በቀስ የሚያድግ፣ ከራስ አልፎ ለሌሎች የሚተርፍ መንፈሳዊ ጸጋ ነው፡፡ ስለዚህ መንፈሳዊነት በራሱ ደረጃ አለውና ለታይታ ሳይሆን ለራሳችን ብለን እንደ አቅማችን ልንጸልይ ይገባል፡፡ “በምትጸልዩበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትሁኑ፣ እነርሱ ለሰው ይታዩ ዘንድ በምኩራብና በአደባባይ መዓዘን መቆምና መጸለይን ይወዳሉና፣ እውነት እውነት እላችኋላሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል” እንደተባለ፡፡ (ማቴ.፮.፭)፡፡

፮. ከችኮላ መራቅ፡-

ለጸሎት በእግዚአብሔር ፊት በቆምን ጊዜም ራሳችንን አረጋግተን በተመስጦ ሆነን መጸለይ ያስፈልጋል፡፡ መቸኮል በማንኛውም የሕይወት ውጣ ውረድ ውስጥ ቢሆን ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል፡፡ የቆምነው በእግዚአብሔር ፊት እንደሆነና የምንነጋገረውም ከእግዚአብሔር ጋር መሆኑን በማሰብ ጸሎትን ሊያቋርጡ ከሚችሉ ነገሮች ከሥጋዊ ፍላጎትና ከንቱ ሐሳብ ርቀን ራስን መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ ጸሎት በዘፈቀደ የሚፈጸም ሳይሆን ዓላማ ኖሮት መከናወን አለበት፡፡ የጀመሩትን ጸሎትም ሳይጨርሱ ጉዳይ አለብኝ፣ እንቅልፍ መጣብኝ፣ አሞኛል የመሳሳሉትን ምክንያቶች በመደርደር ለማረፍ መቸኮል ወይም ለሌላ ጉዳይ ተጣድፎ ማቋረጥ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህንን ድርጊት ከመፈጸምም መቆጠብ ከአንድ ክርስቲያን ይጠበቃል፡፡ በችኮላ የምንገነባው ማንኛውም ነገር አወዳደቁ የከፋ ስለሚሆን ከችኮላ መራቅ አለበት፡፡

እነዚህ ከላይ ያየናቸው ነጥቦች ከብዙው በጥቂቱ ሲሆን በሚቀጥለው በክፍል ፭ ዝግጅታችን ደግሞ የጸሎት ሰዓታትን እንመለከታለን፡፡ ይቆየን፡፡

 

 

 

 

 

 

 

“የጽድቅንም ጥሩር ልበሱ”/ኤፌ.፮.፲፬/

በእንዳለ ደምስስ

ክፍል ሦስት

“የጽድቅንም ጥሩር ልበሱ” በሚል ርእስ በክፍል አንድ ዝግጅታችን ስለ ጾም በጥቂቱም ቢሆን ያቀረብን ሲሆን በክፍል ሁለት ደግሞ ጸሎትና የጸሎት ጥቅሞችን ማየት ጀምረን እንደነበር ይታወሳል፡፡ በክፍል ሁለት ዝግጅታችንም የጸሎት ጥቅሞችን በተመለከተ ከተጠቀሱት ውስጥ፡- በጸሎታችን ስለተደረገልን ሁሉ ምስጋና ማቅረብ፣ ስለ በደላችን ይቅርታን እናገኛለን፣ እንዲሁም መንፈሳዊ ኃይልን እናገኛለን በሚል አቅርበን ነበር፡፡ ቀሪዎቹ የጸሎት ጥቅሞችን ደግሞ ቀጥለን እናቀርባለን፡፡

. . .የጸሎት ጥቅሞች፡-

ምሥጢር ይገለጽልናል፡- ምሥጢር አመሥጠረ፣ አራቀቀ ካለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጉሙም ረቂቅ፣ የማይታይ፣ ኅቡእ፣ ሽሽግ፣ ማለት ነው፡፡ ምሥጢር የሰው ልጅ በራሱ ጥበብ መርምሮ ሊደርስበትና ሊያውቀው የማይችል፣ በእግዚአብሔር ፈቃድ ብቻ ሊገለጥ የሚችል ነው፡፡ “ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና” እንዲል(ዮሐ.፲፭.፭)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በባሕር ላይ በታንኳ ወጥቶ ሳለ ብዙ ሰዎች ወደ እርሱ ተሰበሰቡ፡፡ ጌታችንም የሰዎቹን መሰብሰብ በተመለከተ ጊዜ ስለ ዘርና ዘሪው በምሳሌ አስተማራቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ቀርበው “ስለምን በምሳሌ ትነግራቸዋለህ?” አሉት፡፡ ጌታችንም ለደቀ መዛሙርቱ “ለእናንተ የመንግሥተ ሰማያትን ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቶአችኋል፣ በውጭ ላሉት ግን በምሳሌ ይሆንባቸዋል” አላቸው፡፡ (ማቴ.፲፫.፲፩፤ ማር.፬.፲፩)፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ከእርሱ ጋር እየዋሉ እያደሩ የቃሉን ትምህርት፣ የእጁን ተአምራት እየተመለከቱ ኖረዋልና የመንግሥተ ሰማያትን ምሥጢር የማወቅ ጥበብ እንደሰጣቸው ነግሯቸዋል፡፡ ስለዚህ ወደ እግዚአብሔር ለቀረቡና እንደ ቃሉም ለሚጓዙ እንደ አቅማቸውና መንፈሳዊ ጥንካሬያቸው ምሥጢርን ይገልጻልና ለሕዝቡም በሚገባቸውና በሚረዱት ምሳሌ ገልጾ አስተማራቸው፡፡

ሰው ከወዳጆቹ፣ ከሚወዳቸውና ከሚወዱት በውስጡ የያዘውን(የደበቀውን) ምሥጢር ነው ብሎ የያዘውን ጉዳይ ገልጾ ላይናገር ይችላል፡፡ ለሌሎች ፍቅር አለኝ ቢልም እንኳን ሸሽጎ የሚያስቀምጠው ምሥጢር ይኖረዋል፡፡ ነገር ግን ከሰዎች ቢደበቅም ከእግዚአብሔር ሊሰወር አይቻለውም፡፡ እግዚአብሔር ግን ለመረጣቸውና ለፈቀደላቸው ብቻ በሚችሉት መጠን ምሥጢርን የሚገለጥ ነው፡፡ ለተመረጡት ስንል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን ይገልጥላቸው ዘንድ ከዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት መካከል ጴጥሮስን፣ ዮሐንስንና ያዕቆብን መርጦ ወደ ታቦር ተራራ እንደወሰዳቸው ቅዱስ ወንጌል ያስተምረናል፡፡ ሌሎቹን ግን በእግረ ደብር ትቷቸው ሦስቱን ብቻ ይዞ ሲወጣ ቀሪዎቹ እኛን ከምሥጢሩ ሸሸገን ብለው ከመከተል ወደ ኋላ አላሉም፣ እነርሱ ተለይተው በመቅረታቸው ስላላዘኑም ለሦስቱም ረቀ መዛሙርት የተገለጸው ምሥጢር ለቀሩትም ተገልጾላቸዋል፡፡ “ከስድስት ቀንም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ወንድሙ ዮሐንስን ይዞ ለብቻቸው ወደ ረጅም ተራራ አወጣቸው፡፡ መልኩም በፊታቸው ተለወጠ፣ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፣ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ፡፡ እነሆ ሙሴና ኤልያስም ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው”(ማቴ.፲፯.፩) እንዲል፡፡ ምሥጢር ዝም ብሎ አይገለጥም በመንፈሳዊ ሕይወት መጋደል፣ ዲያብሎስንም ድል የምንነሣበት ዕቃ ጦር መያዝ ያስፈልጋል፡፡ ከእነዚህም መንፈሳዊ መሣሪያዎች ውስጥ አንዱ ጸሎት ነው፡፡ ስለዚህ በጸሎት መትጋት ከእኛ ክርስቲያኖች ይጠበቃል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ቆላስይስ በላከው መልእክቱ “ስለ እርሱ የታሰርሁለትን የእግዚአብሔርን ምሥጢር እንድናገር እግዚአብሔር የቃሉን በር ይከፍትልን ዘንድ ለእኛም ደግሞ ጸልዩልን፣ ለምኑሉንም፡፡ ልናገርም እንደሚገባኝ እገልጠው ዘንድ ጸልዩልኝ” እያለ ሲማጸን እንመለከታለን፡፡ ይህም የእግዚአብሔር ቃል ምሥጢሩን ተረድተን፣ እንደሚገባው እንዲገለጥና ለሌሎች ብርሃን ለመሆን ጸሎት ምን ያህል ዋጋ እንዳለው ያሳየናል፡፡

ከፈተና እንድናለን፡- ፈተና በተለያዩ ምክንያቶች ሊመጣ ይችላል፡፡ የማይገባንን ምኞት በመመኘትና ይህንንም ለማሳካት በምናደርገው ውጣ ውረድ ውስጥ ወደ ማንወጣው ፈተና ውስጥ እንገባለን፡፡ ቅዱስ ዳዊት የጦር አለቃውን የኦርዮንን ሚስት በማይገባ ሁኔታ ተመኘ፣ ምኞቱንም ለማሳካት ባደረገው ጥረት ውስጥ ወደ ሌላ ፈተና ተሸጋገረ፡፡ ከቤርሳቤህ ጋር ዝሙትንም ፈጸመ፣ ኦርዮንንም እስከማስገደል አደረሰው፣ በዚህ አላበቃም በኃጢአት የተወለደውንም ልጅ በሞት አጣ፣ እግዚአብሔርንም አሳዘነ፡፡ በማይገባ ሁኔታ መመኘቱ ለከፋ ኃጢአት አሳልፎ ሰጠው፣ ፈተናውንም መቋቋም ተሳነው፡፡ በመጨረሻም ወደ ልቡናው ሲመለስ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ፣ በትረ መንግሥቱን ጥሎ ትቢያ ለብሶ፣ ዐመድ ነስንሶ በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ጮኸ፣ ጩኸቱንም እግዚአብሔር ተቀበለው፣ ይቅርም አለው፡፡ (ሳሙ.፲፩ እና ፲፪)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ጌቴሴማኒ ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ሔዶ ከእነርሱ ፈቀቅ ብሎ ይጸልይ ነበር፡፡ ሐዋርያት ግን ከእርሱ ጋር በጸሎት ከመትጋት ይልቅ እንቅልፍ አሸንፏቸው ተኝተው አገኛቸው፡፡ በዚህም ምክንያት “አንድ ስዓት እንኳ ከእኔ ጋር እንዲህ ተሳናችሁን? ወደ ፈተና እንዳትገቡ ተግታችሁ ጸልዩ” ሲል ነግሯቸዋል፡፡ ከፈተና ለመጠበቅም ሆነ ከፈተና ለመውጣት ጸሎት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ያመለክተናል፡፡ (ማቴ.፳፮.፵፩)፡፡ መከራ ሲመጣ መሸሽ ሳይሆን በጽናት በሃይማኖት መቆምን ይጠይቃል፣ በሃይማኖት ለመቆም ደግሞ ጸሎት እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገዳመ ቆሮንቶስ ዲያብሎስን ድል እንዳደረገው አባቶቻችንም አምላካቸውን አርአያ አድርገው በጸሎት በመትጋት ፈተናውን ታግሠው ድል ነስተው ተሻግረውታልና እኛም አባቶቻችንን አብነት አድርገን ተግተን መጸለይ ይገባል፡፡ ፍጻሜው መንግሥተ ሰማያት ነውና፡፡

የጎደለንን እናገኛለን፡- የሰው ልጅ በዚህ ምድር ላይ አንዱ ሲሞላለት ሌላው ሲጎድልበት በድካም ይኖራል፡፡ የጎደለውን ለማግኘትም ሰማይን ካልቧጠጥኩ፣ ምድርን ካልቆፈርኩ እያለ ይባዝናል፡፡ ይህ ደግሞ ከንቱ ድካም ነው፡፡ ነገር ግን ሥጋዊ ፍላጎታቸውን በመግታት፣ በጸሎት በመትጋት የጎደላቸውን መንፈሳዊ ሕይወት ይሞላላቸው ዘንድ አምላካቸውን እየተማጸኑ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ትእዛዛት ያስገዙ ቅዱሳን፣ ፃድቃን ሰማዕታት ይህንን ኃላፊውን ዓለም ድል ነሥተውታል፣ የጎደላቸውንም አግኝተዋል፡፡

የጎደለንን ለማግኘት በእግዚአብሔር መታመንን ይጠይቃል፣ ዘወትር በዓለማዊው ጥበብ ያጣነውን ለማግኘት ከመማሰን ወደ እግዚአብሔር በመጸለይ የሚገኘውን በረከት መጠበቅ መልካም ነው፡፡ ሳምራዊቷ ሴት ጎዶሎዋን ይሞላላት ዘንድ፣ ዳግመኛም ወደ ወንዝ እየወረደች ውኃ እንዳትቀዳ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ተማጽናለች፡፡ “ጌታ ሆይ እንዳልጠማ ዳግመኛም ውኃ ልቀዳ ወደዚህ እንዳልመጣ እባክህን ከዚህ ውኃ ስጠኝ” ስትል ጌታችንን የጎደላትን ነገር ጠየቀችው፡፡ (ዮሐ.፬.፲፭)፡፡

በቅድሚያ የጎደለንን ነገር ለይተን እንወቅ፣ የጎደለንን ለማግኘትም እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ በጸሎት መትጋት ከእኛ ኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡ ሕዝቅያስ ታሞ ለሞትም በደረሰ ጊዜ በልቅሶና በዋይታ ከሞት ያድነው፣ ጤናውንም ይመልስለት ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፣ እግዚአብሔርም የሕዝቅያስን ጸሎት ተቀብሎ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስን ልኮም “የአባትህ የዳዊት አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፣ ጸሎትህን ሰምቻለሁ፣ ዕንባህንም አይቻለሁ፣ እነሆ እኔ እፈውስሃለሁ፣ . . . በዕድሜህም ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት እጨምርልሃለሁ” ሲል ተናግሮታል፡፡ ያጣነው ጤና ቢሆን፣ የመንፈሳዊ ሕይወት ጉድለት ቢሆን፣ . . . ጉድለታችን ወደሚሞላው ወደ እግዚአብሔር በመጸለይ ነው፡፡ ሕዝቅያስ ጸልዮ እንደተከናወነለት እኛም ብንጸልይ እግዚአብሔር ይሰማናል ጉድለታችንንም ሞልቶ ይሰጠናል፡፡(፪ነገ.፳.፭)፡፡

ይቆየን፡፡

“የእግዚአብሔር ልጅ የመሆን ሥልጣን (ዮሐ.፩፥፲፪)

መ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

የእግዚአብሔር ልጅ የመሆን ሥልጣን የሚገኘው በእግዚአብሔር ቸርነት እንጂ በራስ ጥረትና በሹሙኝ ቅስቀሳ አይደለም፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደገለጸው “ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣንን ሰጣቸው”(ዮሐ.፩.፲፪) በማለት ለተቀበሉት እና ላመኑት በጸጋ የሚሰጥ መሆኑን አስረድቷል፡፡ ይህም የሚገኘው ዳግም ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማሕፀነ ዮርዳኖስ በመወለድ ነው፡፡

ዳግም ልደት ማለት ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ማለትም ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ፣ ከማኅፀነ ዮርዳኖስ መወለድ ሲሆን፣ የሥላሴ ልጅነትን ያስገኛል፡፡ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወንዱ በተወለደ በዐርባኛው ቀን፣ ሴቷ በተወለደች በሰማንያ ቀኗ ዳግም ከውኃና ከመንፈስ እንዲወለዱ ታደርጋለች፡፡ ለዚህም መነሻዋ መጽሐፍ ቅዱስን አስረጅ በማድረግ  አዋልድ መጻሕፍትን እና ትውፊታዊ አስተምህሮዋን ተከትላ ነው(ኩፋ.፬፥፱)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሌሊት ወደ እርሱ እየመጣ ይማር ለነበረው ለኒቆዲሞስ ስለ ዳግም ልደት ሲያስተምረው እንዲህ አለው፡፡ “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” ካለው በኋላ ኒቆዲሞስ ስላልገባው በነገሩ ግራ በመጋባቱ ሰው ዳግመኛ እንዴት መወለድ ይችላል? ሲል ጠየቀው፡፡ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፡፡ “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነውና፤ ከመንፈስ የተወለደ መንፈስ ነውና” (ዮሐ.፫፥፫-፮) በማለት አስረዳው፡፡

የሰው ልጅ ዳግም ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ሲወለድ የእግዚአብሔር ልጅ ይሆናል፡፡ መንፈስ ቅዱስም ስለሚያድርበት የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ ለእግዚአብሔር የተለየ ዙፋን፣ የእግዚብሔር ቤተ መቅደስ ይባላል፡፡ በዘመነ አበውም ሆነ በዘመነ ኦሪት ራሳቸውን ከርኩሰትና ከኃጢአት ለይተው ለእግዚአብሔር ክብር ከተለዩ ምእመናን ጋር እግዚአብሔር በረድኤት ነበረ፡፡

በሐዲስ ኪዳንም የእግዚአብሐር ልጅ የመሆን ሥልጣንን ያገኘ ሰው አካሉ የመንፈስ ቅዱስ ቤት ማደሪያ ይሆናል፡፡ ይህንን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የሆነ አካል በንጽሕና በቅድስና መያዝ የሚያድርበትን እግዚአብሔርን ማክበር ነው፡፡ እግዚአብሔር ንጹሐ ባሕርይ ነውና ያድርበት ዘንድ ንጹሕ ነገርን ይወዳል፡፡ በኃጢአትና በበደል በተጐሳቆለ አካል ላይ እግዚአብሔር አያድርም፡፡ የእርሱ ማደሪያ፣ ለመሆን በኃጢአት ያደፈውን ማንነት በንስሓ ማጠብና ማንጻት ያስፈልጋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች በላከላቸው መልእክቱ “ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር ለተቀበላችሁት በእናንተ አድሮ ላለ ለመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን? ለራሳችሁ አይደላችሁም በዋጋ ተገዝታችኋልና ስለዚህም እግዚአብሔርን በሥጋችሁ አክብሩት” (፩ኛቆሮ ፮፥፲፱) ይላልና፡፡

ሐዋርያው እንደገለጸው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የተሰቀለውና ደሙን ያፈሰሰው በዲያብሎስ ግዛት ሥር ወድቆ የነበረውን፤ የሰው ልጅ ነጻ ለማውጣት ነው፡፡ በሲኦል የነፍስ መገዛትን፤ በመቃብር የሥጋን መበስበስ፣ አስወግዶ በፊቱ ሕያዋን አድርጎ ሊያቆመን ስለ በደላችን የደሙን ዋጋ ከፍሎ ገዝቶናልና የራሳችን አይደለንም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ በመሆን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ መሆናችን እያስተዋልን ከኃጢአት ልንርቅና ከበደል ልንነጻ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ፡-
“እናንተ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆናችሁ የእግዚአብሔር መንፈስም በእናንተ ላይ አድሮ እንደሚኖር አታውቁምን? የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ የሚያፈርሰውን ግን እርሱን ደግሞ እግዚአብሔር ያፈርሰዋል፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነውና፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስም እናንተ ራሳችሁ ናችሁ፤ እንግዲያስ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ አታርክሱ”   (፩ኛቆሮ.፫፥፲፮)ያለን፡፡

የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መሆን እጅግ የከበረ ማንነት ነው፡፡ ይህም የሚያሳየው እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ምን ያህል እንዳከበረውና እንደወደደው ነው፡፡ ለሰው ልጅ ወደር የሌለው ፍቅሩን የገለጠበትም ታላቅ ምሥጢር ነው፡፡ እግዚአብሔርን ያህል በባሕርዩ ቅዱስ የሆነ ጌታ በእኛ በደካሞችና፣ በበደለኞች አካል ማደሩ እጅግ የሚያስደንቅ ቸርነት ነው፡፡ ይህንን ስንረዳ እግዚአብሔር ለእኛ ያደረገውን ምሕረት እናደንቃለን፡፡

በወንጌል እንደ ተጻፈው በእርሱ ሕይወት ይሆንልን ዘንድ የሚወደውን አንድያ ልጁን ወደ ጎስቋላዋ ዓለም ልኮታል፡፡ “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ሕይወት እንዲያገኝ እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ቤዛ አድርጎ እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲህ ወዶታልና”(ዮሐ.፫፥፲፮)፡፡

እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍጹም ፍቅሩን ማስተዋል ከቻልን የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ የሆነ አካላችንን የኃጢአት መሣሪያ ለማድረግ አንደፍርም፡፡ ምክንያቱም ቀደም ብለን እንዳየነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “በዋጋ ተገዝታችኋልና የራሳችሁ አይደላችሁም” በማለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዋጋ የገዛን ገንዘቡ እንደሆንን አስገንዝቦናል፡፡

የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ከተረዳን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ እንደሆንን መገንዘብ አለብን፡፡ ይህንን ከተረዳን ደግሞ አካላችን በኃጢአት ማቆሸሽ እንደሌለብን፤ በንጽሕና በቅድስና መኖር እንደሚገባን አውቀን ራሳችንን በንስሓ ታጥበን ንጹሓን መሆን ይገባናል፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች ነንና ስለ ኃጢአታችን እንዳይፈረድብን አካሎቻችንን ሁሉ ለእግዚአብሔር አገልግሎት ልናውላቸው ያስፈልጋል፡፡

አንዳንድ ሰዎች ግን ይህንን ባለ መረዳት ሰውነታቸውን ሲያረክሱና ሲያቆሽሹ ራሳቸውን ከእንስሳት በታች ሲያደርጉ ይታያሉ፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት የሰው ልጅ ቢያውቅበት ምንኛ ታላቅ እንደሆነ በመዝሙሩ ሲገልጽ፡- “ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አላወቀም፣ ልብ እንደሌላቸው እንስሶችም ሆነ፣ መሰላቸውም” (መዝ.፵፰፥፲፪)ይላል፡፡

የሰው ልጅ ክብሩ(የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑ) እውን የሚሆነው ያከበረውን እግዚአብሔርን በሰውነቱ ማክበርና፣ አካሉ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መሆኑን ተረድቶ ከኃጢአት ሲለይ ብቻ ነው፡፡ ሰው በጥምቀት የእግዚአብሔር ልጅ የመሆን ሥልጣንን ስለሚያገኝ ከእግዚአብሔር ቸርነት የተነሣ የተቀደሰና የተከበረ ነው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ “ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣንን ሰጣቸው፤ እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከሥጋዊና ከደማዊ ግብር ወይም ከወንድና ከሴት ፈቃድ አልተወለዱም” (ዮሐ.፩፥፲፪)ያለው፡፡

የእግዚአብሔር ልጅ የመሆንን ሥልጣን የተሰጣቸው ሁሉ ድካም ገጥሟቸው ኃጢአትን በመሥራት የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የሆነ አካላቸውን በሚያሳድፉበት ወቅት ወዲያውኑ ንስሓ በመግባት ከኃጢአት መንጻት አለባቸው፡፡ ንስሓ ኃጥኡን ጻድቅ፣ ዘማዊውን ድንግል ያደርጋልና፡፡ ኃጢአትን የሠሩ ምእመናን ንስሓ በገቡ ጊዜ ከኃጢአታቸው ይነጻሉ፡፡ በሚነጹበትም ጊዜ ንጹሓን የእግዚአብሔር ማደሪያዎች ናቸውና ቅዱሳን ይባላሉ፡፡
የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡ አሜን፡፡

በጊዜው ሁሉ ጸልዩ(ፊል.፬.፮)

ክፍል ሁለት

በእንዳለ ደምስስ

ጸሎት ጸለየ፣ ለመነ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲሆን መለመን፣ ማመስገን፣ በንጽሕና በእግዚአብሔር ፊት መቆም፣ ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር ማለት እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ “ጸሎትስ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር የሚናገርባት ናት” (ፍትሐ. ነገ. አንቀጽ ፲፬) እንዲል፡፡

አዳም አባታችን ተግቶ በመጸለዩ ዲያብሎስ ሊፈትነው በቀረበ ጊዜ ድል ነስቶታል፣ ሔዋን ግን ሥራ ፈትታ፣ እግሯን ዘርግታ በመቀመጧ በቀላሉ በዲያብሎስ ተረትታለች፣ ዕፀ በለስንም በልታ አጋርዋን አዳምን እስከማብላት ደርሳለች፡፡ በዚህም ምክንያት የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ተላልፈዋልና ተረግመው፣ ስደተኛ ሆነው ከገነት ተባረሩ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ተግተን መጸለይ እንደሚገባን ሲያስረዳ ለፊልጵስዩስ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ “እግዚአብሔር ቅርብ ነው፣ ምንም ምን አታስቡ፣ ነገር ግን በጊዜው ሁሉ ጸልዩ፣ ማልዱ፣ በምታመሰግኑበትም ጊዜ ልመናችሁን ወደ እግዚአብሔር አቅርቡ” ይለናል፡፡ ዲያብሎስን ድል መንሣት የምንችለውም በጸሎት ኃይል እንደሆነ አስረድቶናል፡፡(ፊል.፬.፮)፡፡

ጸሎት ለመንፈሳዊ ሰው አስፈላጊና ትልቁ መሣሪያው ሊሆን ይገባል፡፡ በዓለም ውስጥ ያለን ሰው  በመውጣት በመውረድ፣ ጥሮ ግሮ ይበላ ዘንድ በታዘዘው መሠረት በርካታ ነገሮች ማለትም በጎም ሆነ መጥፎ ነገር ሊገጥመው ይችላል፡፡ ለገጠመው ክፉ ነገር እግዚአብሔር ችግሩን እንዲያስወግድለት በትጋት መጸለይ፣ እንዲሁም ለተደረገለት መልካም ነገር ሁሉ በጸሎት እግዚአብሔርን ማመስገን ይገባዋል፡፡ ብዙውን ጊዜ በደስታችን ወቅት ሳይሆን በችግራችን ጊዜ እግዚአብሔርን ለመፈለግ ጥረት ስናደርግ እንታያለን፡፡ ነገር ግን በጊዜውም ያለጊዜውም  ቢሆን ወደ እግዚአብሔር መጸለያችንን መቀጠል ያስፈልጋል፡፡  እርሱንም መለመንና ማመስገን ለሰው ልጅ የተሰጠ ስጦታ ነውና፡፡

ለመሆኑ በጸሎት ምን እናገኛለን? ጥቅሙስ ምንድነው? ቀጥለን እንመለከታለን፡-

የጸሎት ጥቅም

ስለተደረገልንና ለሚደረግልን ሁሉ ምስጋና ለማቅረብ፡- ከላይ እንደጠቀስነው በችግራችን ጊዜ ብቻ ሳይሆን በደስታችንም ጊዜ ለእግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ ከአንድ ክርስቲያን ይጠበቃል፡፡ ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ ተቀብለኸኛልና የጠላቶቼ መዘባበቻ አላደረግኸኝምና አመሰግንሃለሁ” በማለት ምስጋና ሲያቀርብ እንመለከታለን፡፡(መዝ.፳9.፩)፡፡ ምስጋና ማቅረብ በእግዚአብሔር እንድንታመን፣ የነገ መንፈሳዊ ሕይወታችን እንዲቃና ያለው ጥቅም ከፍተኛ ነው፣ ተስፋ ከመቁረጥ ይታደገናልና፡፡ ተስፋ ባለመቁረጥ የምናቀርበው የምስጋና ጸሎት ደግሞ በእግዚአብሔር ፊት ዋጋ ስላለው ዘወትር መትጋት ይጠበቅብናል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች በላከው ሁለተኛው መልእክቱ “ስለማትመረመርና ባላሰቡአት ጊዜ ስለምትመጣው ጸጋው እግዚአብሔር ይመስገን” እንዲል(፪ቆሮ.9.፲፭)፡፡

ስለበደላችን ይቅርታን እናገኛለን፡- ይቅርታ ከዚህ በፊት ስለተፈጸመና ወደፊት ደግመው ሊያደርጉት በማይገባ በደል ምክንያት የሚጠየቅ ትሕትናን የተላበሰ፣ በተሰበረ መንፈስ ለተበዳይ የሚቀርብ ነው፡፡ ሰዎችን ብንበድል ከእግዚአብሔር ትእዛዝ አፈንግጠናልና በማይገባ መንገድም ተጉዘናልና ተበዳዩን ግለሰብ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔርንም ጭምር ነው ያሳዘንነው፡፡ ስለዚህ ለፈጸምነው በደል በግለሰቡ ፊት ወድቀን ይቅርታ ስንጠይቅ ግለሰቡም እግዚአብሔርም ይቅርታውን ይቀበላሉ፡፡ “ይህን አስቡና አልቅሱ፣ የተሳሳታችሁ ሆይ ንስሓ ግቡ፣ ልባችሁንም መልሱ” ይለናል(ኢሳ.፵፮.8)፡፡ ልብን መመለስ፣ በቀናውም መንገድ መጓዝ ቀድሞ ስለበደሉት በደል መጸጸትና ማልቀስ፣ በተሰበረ ልብም ሆኖ ይቅርታ መጠየቅ ተገቢ መሆኑን ያስረዳናል፡፡ መዝሙረኛው ዳዊት “አንተን ብቻ በደልሁ፣ በፊትህም ክፋትን አደረግሁ፣ በነገርህ ትጸድቅ ዘንድ በፍርድህም ታሸንፍ ዘንድ” እያለ ስለ በደሉ ይቅርታ ሲጠይቅ እናያለን፡፡ (መዝ.$..፬)፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤልም “ማቅ ለብሼ በዐመድም ላይ ሆኜ ስጾም እጸልይና እለምን ዘንድ ፊቴን ወደ ጌታ ወደ አምላክ አቀናሁ፡፡ ወደ አምላኬም ወደ እግዚአብሔር ጸለይሁ … አቤቱ ስማ፣ አቤቱ ይቅር በል፣ አቤቱ  አድምጥና አድርግ አምላኬ ሆይ ስምህ በከተማህና በሕዝብህ ላይ ተጠርቷልና ስለ ራስህ አትዘግይ” እያለ እግዚአብሔርን ይማጸናል ይቅር ማለት የሚችል እግዚአብሔር ነውና፡፡ ይቅርታ የኅሊና ዕረፍትን ይሰጣል፣ ይቅርታ ለአድራጊውም፣ ለተደረገለትም ሰላማዊ ግንኙነታቸውን የሚቀጥሉበት የሰላም ድልድይ ነው፡፡ ከኅሊናችን ጋር ታርቀን፣ ንስሓ ገብተን የወደፊት ሕይወታችንን ልንመራ የምንችለው ይቅርታን ስናገኝና እኛም የበደሉንን ይቅር ስንል ነው፡፡ ጸሎታችንም ይህ ሊሆን ይገባል፡፡ “አምናችሁ በጸሎት የምትለምኑትን ሁሉ ታገኛላችሁ” እንዲል(ማቴ.፳፩.፳፪)፡፡

ንጉሡ ሕዝቅያስ በታመመና ለሞትም በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ነቢዩ ኢሳይያስን ልኮ “ትሞታለህ እንጂ በሕይወት አትኖርምና ቤትህን አስተካክል” አለው፡፡ ሕዝቅያስም ይህንን በሰማ ጊዜ ፊቱን ወደ ግድግዳ አዙሮ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡- “አቤቱ በፊትህ በእውነትና በፍጹም ልብ እንደሄድሁ፣ መልካም ነገርንም እንዳደረግሁ አስብ” በማለት አልቅሷል፡፡ እግዚአብሔርም የሕዝቅያስን ጸሎት ተቀበለ፡፡ እንዲህም አለው፡- “ጸሎትህን ሰምቻለሁ፣ ዕንባህንም አይቻለሁ፣ እነሆም እኔ እፈውስሃለሁ፣ … በዕድሜህም ላይ አሥራ አምስት ዓመት እጨምርልሃለሁ” ሲል መልካሙን ዜና ለመስማት በቅቷል፡፡(፪ኛ ነገ.፳.፩)፡፡ ስለዚህ በጸሎት ኃይል ይቅርታን እናገኛለን፡፡

መንፈሳዊ ኃይልን እናገኛለን፡- መንፈሳዊ ኃይል በአንድ ጀምበር የሚገኝ አይደለም፡፡ ማመን፣ ለአመኑትም አምላክ መገዛት፣ ዘወትር በሚያምኑት አምላክ ፊት መቆምንና መጸለይን ይጠይቃል፡፡ መንፈሳዊ ኃይል መንፈሳዊ ልምምድ በማድረግ፣ በጸሎት በመበርታት የሚገኝ ጸጋ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ “እርስ በእርሳችሁ ኃጢአታችሁን ተናዘዙ፣ እንድትድኑም ለወንድሞቻችሁ ጸልዩ፣ የጻድቅ ሰው ጸሎቱ ብዙ ትረዳለች፣ ግዳጅም ትፈጽማለች” ይላል ከራስ አልፎም ስለ ሌሎች መጸለይ እንደሚገባ ሲያስረዳን፡፡(ያዕ.፲፭.፲፮)  ይህም ከእግዚአብሔር የሚሰጥ ጸጋ ነውና፡፡ ጸሎት በንጹሕ ኅሊና ሆነው ቢጸልዩ “ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ” እንዲል ቅዱስ ዳዊት የለመኑትን የማይነሣ አምላክ በጸጋ ላይ ጸጋንም ያላብሰናል፡፡(መዝ.፻፵፥፪)፡፡ ይቆየን፡፡

“የሰላም መንገድ” (መዝ.፲፬፥፮)

በመ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

ሰላም ማለት ጸጥታ፣ ዕረፍት፣ እርጋታ፣ እርካታ ማለት ሲሆን የእርስ በእርስ ስምምነት፣ በአንድነት አብሮ መኖር፣ መቻልና የዕረፍት ስሜት እንደሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ያስረዳል፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ክፉዎች የሰላምን መንገድ የማያውቁ መሆናቸውን “ደምን ለማፍሰስ እግራቸው ፈጣን ነው፣ ጥፋትና ጉስቁልና በመንገዳቸው አለ፣ የሰላምን መንገድ አላወቁአትምና እግዚአብሔርን መፍራት በዓይናቸው ፊት የለም” (መዝ.፲፬፥፮) ሲል ይገልጻል፡፡

በሌላም ክፍል በጎ ዘመንን ሊያይ የሚወድ ቢኖር ሰላምን መፈለግና የሰላምን መንገድ መከተል እንደሚገባው ሲያስረዳን፡- “ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችሁ ዘንድ፤ ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎ ዘመንንም ለማየት የሚወድድ ማን ነው? አንደበትህን ከክፉ ከልክል፣ ከንፈሮችህም ሸንገላን እንዳይናገሩ ከክፉ ሽሽ፣ መልካንም አድርግ፣ ሰላምን ሻት ተከተላትም” በማለት ሰላምን መከተል እንደሚገባ ያስረዳናል፡፡ (መዝ.፴፫፥፲፫-፲፬)

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ልጆቹ ለምንሆን ለእኛ ሲያስተምረን እግዚአብሔር የፈቀደለትንና እርሱ በሕይወቱ ገንዘብ አድርጎት በእግዚአብሔር እንደ ልቤ ተብሎ የተመረጠበትን ጥበብ ሲነግረን “እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁ” አለ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔርን መፍራት ከሁሉ ይልቅ ቀዳሚ ነውና፡፡ ለዚህም ነው አባትና ልጅ ተባብረው(ተቀባብለው) የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት እንደሆነ የነገሩን (መዝ.፻፲፥፲፤ ምሳ.፩፥፯፤9፥፲)፡፡

ከሁሉ አስቀድሞ በሕይወታችን እግዚአብሔርን መፍራት አስፈላጊ ነው፡፡ ሰላምን የምንሻበት መንገድ እርሱ ነውና፡፡ ቅዱስ ዳዊት እግዚአብሔርን መፍራት ሕይወትን የሚያስገኝና በጎ ዘመንን ለማየት የምንችልበት የጥበብ (የዕውቀት) ሁሉ መሠረት እንደሆነ ከገለጸ በኋላ “ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎ ዘመንንም ለማየት የሚወድድ ማን ነው?” ብሏል፡፡ ከላይ እንዳየነው ሕይወትን ለማግኘት የሚሻ በጎ ዘመንንም ለማየት የሚፈልግ ጥበብን (ማስተዋልን) ገንዘብ ያደረገ ሰው ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት እንደነገረን የሰላምን መንገድ መከተል፣ ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንን ለማየት የሚሻ ሰው ምን ማድረግ እንዳለበት ስንመለከትም፡-

ኛ. አንደበትን  ከክፉ መከልከል፡-

የሰው ልጅ በልቡ ያሰበውን በአንደበቱ ይናገራል፡፡ በልብ የታሰበውን መልካምም ይሁን ክፉ የሚያውቀው እግዚአብሔር ብቻ ሲሆን፣ ነገር ግን የታሰበው ነገር በውጫዊ ሰውነት ላይ በሚታዩ ምልክቶች(ገጽን በማየት) መታወቅ የሚችልበት አጋጣሚ ከተፈጠረ ወይም በአንደበት ቢነገርና በሥራ ቢተገበር ሰዎች ይረዱት ይሆናል፡፡

አንደበትን ከክፉ ካልከለከሉት ሰዎችን የሚጎዳና የማይሽር ጠባሳ ጥሎ የማለፍ፣ በዚያም ሰበብ ተናጋሪውን ሳይቀር ለሞት የማብቃት ዕድል አለው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ “ምላስም እሳት ናት እነሆ ትንሽ ምላስ በሰውነታችን ውስጥ  ዐመፅ የተመላበት ዓለም ናት ሥጋችንን ትበላዋለች፣ ውስጣዊ ሰውነታችንንም ትጠብሰዋለች፣ ከገሃነምም ይልቅ ታቃጥላለች” በማለት የገለጸው፡፡(ያዕ.፫፥፮) ስለዚህ ሕይወትን የሚፈቅድና በጎ ዘመንን ለማየት የሚፈልግ ሰው አንደበቱን ከክፉ ነገር መከልከልና መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ ተናግሮ ሰውን ላለማስቀየምና ላለማስከፋት መጠንቀቅ፣ ሌላውንም ሰው ወደ ጥፋት ላለመምራት ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ አንደበት ኃያል ነው ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው ይበልጣል ይባላልና፡፡

አንደበትን ከክፉ ካልከለከልነው ስድብንና ሐሜትን እናበዛለን፡፡ ይህ ደግሞ ከሕይወት ጎዳና የሚያወጣ ክፉ ተግባር ነው፡፡ በጓደኛ፣ በባልና ሚስት፣ በአንድ ሀገርና በሌላው ሀገር፣ በጎሳና በጎሳ፣ በጎረቤትና በጎረቤት መካከል ሐሜትና መነቃቀፍ፣ ስድብና ጥላቻ ካለ በጎ ዘመንን ማየት አይቻልም፡፡ ነገር ግን ሕይወትንም ሆነ በጎ ዘመንን ለማየት አንደበትን ከክፉ መከልከልና በጎ ነገርን መናገር አስፈላጊ ነው፡፡

ኛ. ከክፉ መሸሽ፡-

ከክፉ  መሸሽ  ማለት  ክፉን  ከማድረግ  መቆጠብና  ክፉ  ከሚያደርጉት  ጋር  በክፋታቸው አለመተባበር ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ሁል ጊዜም ቢሆን ከክፉዎች ጋር ኅብረት የለውም፡፡ አባታችን ያዕቆብ ልጆቹን በሚመርቅበት ጊዜ ክፉ ሥራ ከሠሩ ከልጆቹ የክፋት ሥራ ጋር እንደማይተባበርና ከክፋት ጋር ኅብረት እንደሌለው ገልጧል፡፡ “ስምዖንና ሌዊ ወንድማማቾች ናቸው፡፡ በጭቅጭቃቸውና በጦራቸው ዐመፅን ፈጸሟት፣ በምክራቸው ሰውነቴ አትገናኛቸው፣ ሐሳቤም በዐመፃቸው አትተባበርም፣ በቊጣቸው ሰውን ገድለዋልና በገዛ ፈቃዳቸውም የሀገርን ሥር ቆርጠዋልና ቁጣቸው ርጉም ይሁን፣ ጽኑ ነገርና ኩርፍታቸውም ብርቱ ነበርና በያዕቆብ እከፋፍላቸዋለሁ በእስራኤልም እበታትናቸዋለሁ” (ዘፍ.፵፱፥፭)፡፡ ያዕቆብ ምንም እንኳ በሥጋ የወለዳቸው ልጆቹ ቢሆኑም በፈጸሙት ክፉ ሥራ ግን እንደማይተባበር ከክፉ ሥራቸው የራቀና ከክፋት የተለየ መልካም ሐሳብ እንዳለው ገልጧል፡፡

ዛሬም ቢሆን የሰው ልጆች ክፋትና በደል እየበዛ ባለበት ሰዓት የእግዚአብሔር ልጆች ከክፋት፣ ከተንኮል፣ ከውሸት፣ ከሌብነት፣ ከቅሚያ፣ ከዝርፊያ፣ ከጭካኔ፣ ከሴሰኝነት፣ ከዘማዊነት፣ ከዘረኝነት በአጠቃላይ ለራስም ሆነ ለሀገር ከማይበጁ እኩይ ምግባራትና ከሚፈጽሟቸው ሰዎች ጋር መተባበር የለብንም፡፡ ቅዱስ ዳዊት እንደነገረን ሕይወትን ለማግኘት የምንሻና በጎ ዘመን ለማየት የምንፈልግ ሁሉ ከክፉዎች ጉባኤ መለየትና አለመተባበር ያስፈልጋል፡፡

ኛ. መልካም ማድረግ

ሕይወትን ለማግኘትና በጎውንም ዘመን ለማየት የሚሻ ሰው ሁሉ መልካምን ሊያደርግ ያስፈልገዋል፡፡ ከክፉ መሸሻችንና ከክፉዎች ጋር አለመተባበራችን መልካም ሥራ ለመሥራት መሆን አለበት እንጂ ከሥራ ርቀን እንዲሁ እንድንኖር አይደለም፡፡ ያለ በጎ ሥራ መኖር ስንፍና ነውና፡፡

እግዚአብሔር የሰውን ውድቀቱንና መጥፋቱን የማይሻ አምላክ ስለሆነ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በክፉ ሥራ ተጠምዶ የነበረ ሁሉ ሊመለስና በሕይወት ሊኖር ይገባዋል፡፡ በቀደመው ስሕተቱ ወንድሙን ያሳዘነ፣ ሰው የገደለ፣ አካል ያጎደለ፣ ግፍን የፈጸመ፣ የድሃውን ገንዘብ በተለያየ ሰበብ የዘረፈ፣ ጉቦ የተቀበለ፣ በእነዚህና መሰል እኩይ ሥራዎች ሀገሩን የጎዳ፣ እግዚአብሔርን የበደለ ሁሉ ከልብ በመጸጸት በልቅሶና በዋይታ ወደ እግዚአብሔር መመለስ ያስፈልገዋል፡፡ ለዚህም አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በነቢዩ ሕዝቅኤል ላይ አድሮ ኃጢአተኛው ከኃጢአቱ ተመልሶ በሕይወት መኖር እንዳለበት አስገንዝቦናል፡፡

“እኔ ሕያው ነኝና ኃጢአተኛው ከመንገዱ ተመልሶ በሕይወት ይኖር ዘንድ እንጂ ኃጢአተኛው (በደለኛው) ይሞት ዘንድ አልፈቅድም፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡ የእስራኤል ቤት ሆይ ተመለሱ ከከፉ መንገዳችሁ ተመለሱ ስለምንስ ትሞታላችሁ?” (ሕዝ. ፴፫፥፲፩) እንዲል፡፡

እግዚአብሔር በነቢዩ ላይ አድሮ እንደ ነገረን በደለኛ ሰው በበደሉ ቀጥሎ መጥፋት የለበትም፡፡ መመለስና በሕይወት መኖት ያስፈልገዋል እንጂ፡፡ እሱም እንደ በደሉ ዓይነት ይቅርታ ጠይቆ፣ ንስሓ ገብቶ፣ የበደለውን ክሶ፣ የሰረቀውን መልሶ፣ የሰበረውን ጠግኖ፣ ያጎደለውን መልቶ በፍጹም መጸጸት ሊመለስና መልካም በመሥራት ሌት ተቀን ከሚተጉት ጋራ በመልካም ሥራ ሊተባበር ያስፈልገዋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን “ስለዚህ ሐሰትን ተውአት ሁላችሁም ከወንድሞቻችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ እኛ አንድ አካል ነንና አትቆጡ፣ አትበድሉም፣ ፀሐይ ሳይጠልቅም ቊጣችሁን አብርዱ፣ ለሰይጣንም መንገድን አትስጡት፣ የሚሰርቅም እንግዲህ አይስረቅ ነገር ግን ድሃውን ይረዳ ዘንድ በእጆቹ መልካም እየሠራ ይድከም” (ኤፌ.፬፥፳፭) ይላል፡፡

ኛ.ሰላምን መሻት

ሰላም ለሁሉ ነገር አስፈላጊና ሁሉን ለማድረግ የምንችልበት የመልካም ነገር ሁሉ በር ነው፡፡ ሰላምን መፈለግ ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንንም ለማየት ያስችላል፡፡ ሰላምን በሁለት መልኩ እናያለን፡፡ እሱም የውስጥ ሰላምና የውጭ ሰላም ወይም ውስጣዊ ሰላምና ውጫዊ ሰላም ተብሎ ይመደባል፡፡

የሰው ልጅ ለመኖር ውስጣዊ ሰላምም ሆነ ውጫዊ ሰላም ያስፈልጉታል፡፡ ውስጣዊ ሰላም የምንለው አንድ ሰው ከፍርሃት፣ ከጭንቀት፣ ከመረበሽ፣ ከሥጋት… ወዘተ ነጻ ሆኖ መኖር ሲችል ውስጣዊ ሰላም አለው ይባላል፡፡ ይህም የውስጥን ሰላም ከሚያደፈርሱ፣ አእምሮን ከሚረብሹ፣ ልብን ከሚያቆስሉ፣ የጸጸት እሮሮን ከሚያስከትሉ ነገሮች ስንርቅና ለአእምሮ የሚመች ሥራ ስንሠራ ውስጣችን ሰላም ይሆናል፡፡

ውጫዊ ሰላም የምንለው ደግሞ፡- ከቤተሰብ፣ ከጓደኛ፣ ከጎረቤት፣ ሀገራት ጋር ተስማምተንና ተግባብተን ተቻችለንና ተረዳድተን በፍቅር ተሳስረን በመኖር ከጥል ከመለያየት፣ ከመጠላላት፣ ከመገፋፋት፣ ከመነቃቀፍ ተቆጥበን የጠብንና የጦርነትን ወሬ ባለመስማትና በስምምነት ተግባብቶ በመኖር የሚገለጥ ነው፡፡ ስለዚህ ሰላም ለሁሉ እንደሚያስፈልገው ካወቅን የሰላም መገኛ ማን እንደሆነና ሰላም ከየት እንደሚገኝ ማወቅ ደግሞ አስፈላጊ ነው፡፡

ሰላም የሚገኘው የሰላም ባለቤት ከሆነው ከልዑል እግዚአብሔር ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንደገለጠው እውነተኛ ሰላም ከእግዚአብሔር ይገኛል፡፡ እርሱ የሰላም አምላክ ነውና (ሮሜ.፲፭፥፴፫)፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰላም አለቃ ተብሏል፡፡ “ሕፃን ተወዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፣ ኃያል አምላክ፣ የዘለዓለም አባት፣ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል” (ኢሳ. 9፥፮) እንዲል፡፡

ዓለም ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ያህል ሰላሙን አጥቶ በመቅበዝበዝ ይኖር የነበረ ሲሆን በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን፣ እውነተኛውን ሰላም አግኝቷል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱ ሞት ምክንያት ፍርሃት ጸንቶባቸው ለነበሩት ደቀ መዛሙርት “ሰላምን እተውላችኋለሁ፣ ሰላሜንም እሰጣችኋለሁ፣ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጠው አይደለም፣ ልባችሁ አይደንግጥ አትፍሩም” (ዮሐ.፲፬፥፳፯) በማለት ፍርሃትን፣ ስጋትን፣ ጭንቀትን፣ ሁከትን፣ መረበሽን የሚያርቀውን (የሚያስወግደውን) እውነተኛውን ሰላም አደለን፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት እንዳለው ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንን ለማየት የምንሻ ሁሉ ሰላምን መሻት ያስፈልጋል፡፡ ደግሞም ሰላምን መሻት ብቻ ሳይሆን መከተል ተገቢ ነው፡፡ ምክንያቱም መሻት ብቻውን ዋጋ ሊኖረው ስለማይችል፡፡ መሻታችን ወደ ማግኘት የሚደርሰው የምንሻውን ነገር ለማግኘት ወደ መገኛው መጓዝና መቅረብ ሲቻል ነው፡፡ ለዚህም ነው ሰላምን ሻት ካለ በኋላ ተከታላትም በማለት በሰላም መንገድ መጓዝ፣ የሰላም ወሬ ማውራት፣ ለሰላም የሚስማማ ሥራ መሥራት፣ የራሳችንን ሰላም መጠበቅና የሌላውንም ሰላም አለማደፍረስ ማለት እንደሆነ የነገረን፡፡ የእግዚአብሔር ሰላም ለሁላችን ይሁንልን፡፡ ይቆየን፡፡