ክርስቲያናዊ ሕይወት ከግቢ ጉባኤያት በኋላ

በመ/ር ተመስገን ዘገዬ

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከብዙ ውጣ ውረድ ማለትም ዓለማዊና መንፈሳዊ ትምህርታቸውን በአግባቡ ከተማሩ በኋላ ተመርቀው ሲወጡ እንዴት መኖር እንደለባቸውና ምን ማድረግ እንደሚገባቸው በዚህ ጽሑፍ ለማሳየት እንሞክራለን፦

፩. ከወንድሞች ጋር በኅብረት መኖር 

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በተሰማሩበት ሁሉ ከማኅበረሰቡ ጋር በኅብረት መኖሩ መልካም ነው፡፡ ክርስትና የኅብረት እንጂ የብቸኝነት ሩጫ አይደለችም፡፡ መጽሐፍም «ወንድሞች በሕብረት ቢቀመጡ እነሆ መልካም ነው፤ እነሆም ያማረ ነው» ሲል መናገሩም ይህንን ያስረዳል፡፡ (መዝ.፻፴፫፥፩)

ጠቢቡ ሰሎሞንም «ድካማቸው መልካም ዋጋ አለውና አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን ይሻላል፡፡ አንዱ ቢወድቅ ሁለተኛው ያነሣዋልና፤ አንድ ብቻውን ሆኖ በወደቀ ጊዜ ግን የሚያነሣው ሁለተኛ የለውምና ወዮለት፡፡» ብሎ እንደተናገረው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በዚህ ዓለም ሲኖሩ በብዙ መንገድ መደጋገፍ ያሻቸዋል፡፡ (መክ.፬፦፱) አንዱ ለሌላው መሥዋዕት  እስከ መሆን ድረስ  አብሮ በፍቅር  መኖር ይገባል፤  የክርስትና ትርጉሙ ይህን  ነውና፡፡ የሞላለትና በሁሉ  ምሉዕ  የሆነ ሰው በዚህ ዓለም ማግኘቱ አስቸጋሪ ሊሆን ስለሚችል መደጋገፍ፣ መረጃ መለዋወጥ  ያስፈልጋል፡፡

በአንድነት መኖር በኢኮኖሚም ለመደጋገፍ፣ እንዲሁም ከተለያዩ የውስጥና የውጭ ፈተናዎች ለመከላከል፣ እንዲሁም ለመጠበቅ ይረዳል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን «ብረት ብረትን ያስለዋል፤ ሰው ባልንጀራውን ይስለዋል፡፡» በማለት መልካም ጓደኛ ሌላውን ጥሩና የተስተካከለ ሰው እንዲሆን እንደሚረዳው ተናግሯል፡፡ (ምሳ.፳፯፥፲፮) መተራረም የሚቻለው በመከባበርና መልካሙን መንገድ በመከተል፤ አንተ ከእኔ ትሻላለህ በመባባል የተሰጠውን አስተያየት በመጠቀም የሕይወት ለውጥ ማምጣት ሲቻል ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት «ከቸር ሰው ጋር ቸር ሆነህ ትገኛለህ፤   ከቅን ሰው ጋር ቅን ሆነህ ትገኛለህ፤ ከንጹሕ  ጋር ንጹሕ  ሆነህ ትገኛለህ» እንዲል፡፡ (መዝ.፲፯፥፳፭)

፪. በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ተካፋይ መሆን፡-

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ የምታድላቸው ሰባት ሀብታት (ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን) አሏት፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን «ጥበብ ቤትዋን ሠራች፥ ሰባቱንም ምሰሶችዋን አቆመች። ፍሪዳዋን አረደች፥ የወይን ጠጅዋን ደባለቀች፥ ማዕድዋን አዘጋጀች። ባሪያዎችዋን ልካ በከተማዪቱ ከፍተኛ ሥፍራ ላይ ጠራች። አላዋቂ የሆነ ወደዚህ ፈቀቅ ይበል፤ አእምሮ የጐደላቸውንም እንዲህ አለች። ኑ፥ እንጀራዬን ብሉ፥ የደባለቅሁትንም የወይን ጠጅ ጠጡ። አላዋቂነትን ትታችሁ በሕይወት ኑሩ፥ በማስተዋልም መንገድ ሂዱ።» በማለት ይገልጻል፡፡ (ምሳ.፱÷፩-፭) በዚህ ቃለ ትንቢት መሠረት ጥበብ የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ቤት የተባለችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ እንዲሁም የክርስቲያኖች ሰውነት ናት፤ ሰባቱ ምሰሶዎች የሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናቸው። የታረደው ፍሪዳ ቅዱስ ሥጋው፣ የተደባለቀው ወይን የክቡር ደሙ ምሳሌ ነው።

በቅዱስ ወንጌል «ኢየሱስም፡- ‘ኑ፥ ምሳ ብሉ’ አላቸው። ከደቀ መዛሙርቱ አንተ ማን ነህ? ብሎ ሊጠይቀወ የደፈረ የለም፤ ጌታችን እንደሆነ አውቀዋልና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መጣና ኅብስቱን   አንሥቶ ሰጣቸው፥ ከዓሣወም እንዲሁ።» ተብሎ እንደተጻፈ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በምንችውለውና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በሚፈቅድልን መሠረት በአገልግሎት መሳተፍ ይጠበቅብናል፡፡ ገና በሥራ ቦታ ተመድበን እንደሄድንም የንስሓ አባት መያዝ፣ በየጊዜው ንስሓ መግባትና እየተገናኘን ቀኖና ተቀብለን ሥጋ ወደሙን መቀበል ያስፈልገናል፡፡ (ዮሐ.፳፩፥፲፪)

በሕይወታችን «የበይ ተመልካች» መሆን አያስፈልግም፡፡ «እውነት እውነት እላችኋለሁ የሰውን ልጅን ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፤ … ሥጋዬን   የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል፤ እኔም በእርሱ እኖራለሁ» እንደተባለ ክርስቲያን  የሆነ ሁሉ  ከዚህ ምሥጢር  በየጊዜው  መሳተፍ  እንዳለበት መረዳት ይገባል፡፡ (ዮሐ.፮፥፶፫-፶፮)

የምንሠራቸው ሥራዎች የሚባረኩት በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምናድገው፣ መንግሥቱንም መውረስ የምንችለው ቅዱስ ሥጋውን ስንበላ፣ ክቡር ደሙንም ስንጠጣ ብቻ ነው፡፡ የምሥጢራት ተካፋይ በመሆን ሌሎችም እንዲካፈሉ ማድረግ ይኖርብናል፡፡

፫. ኑሮን በዕቅድ መምራት፡-

ዕቅድ የሌለው ሁሉ መንገዱ ውጣ ውረድ የበዛበት ነው፡፡ ኑሮዬ ይበቃኛል ብለን መኖር የምንችለው በዕቅድ ስንመራ ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «ስለ ጉድለት አልልም የምኖርበት ኑሮዬ ይበቃኛል ማለትን ተምሬለሁ» ያለው ክርስቲያን ሕይወቱን እንደዚሁ በዘፈቀደ እንደመጣለት መምራት እንደማይገባው ሲያስገነዝበን ነው፡፡ (ፊል.፬፥፲) ዕድሜያችን በዕቅድ ላይ ተመሥርተን በመምራት ካልተጠቀምንበት ምንም ሳንሠራበት ያልቃል፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረቱን ሲፈጥር በአንድ ጊዜ ማከናውን የሚችለውን ስድስት ቀናት የፈጀበት እያንዳንዱን ነገር በዕቅድና በሥርዓት ማከናወን እንደሚገባ ሲያስተምረን ነው፡፡ ሥራ የምንሠራበት፣የምንጸልይበት፣ ትምህርተ ሃይማኖት የምንማርበት፤ ንስሓ ገብተን ቅዱስ ቊርባኑን የምንቀበልበት የራሳችን  ዕቅድ ያስፈልገናል፡፡

የምናገኘው ገንዘብ ያለ ዕቅድና ዓላማ የምናወጣ ከሆነ ከወር ወር መድረስ አንችልም፡፡ ደመወዛችን የተቀበልን ሰሞን ሆቴል የምናማርጥ ከሆነ በወሩ አጋማሽ ጾማችንን ማደራችን የማይቀር ጉዳይ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «ነገር ግን ሁሉ በአገባብና በሥርዓት ይሁን» ይላል (፩ኛቆሮ.፲፬፥፵) የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር የቄሣርን ለቄሣር እንደተባለ በእግዚአብሔር ድርሻ ላይ ታማኞች መሆን አለብን፡፡ ስለሆነም በበረከት እንዲያትረፈርፈን ዐሥራት የማውጣት ልምድ  ከመጀመሪያው ደመወዛችን መጀመርና በየወሩ ዐሥራታችንን ማውጣት ይኖርብናል፡፡

፬. በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በአገልግሎት መሳተፍ

ልዑል እግዚአብሔርን ማገልገል የምንችለው በቤተ ክርስቲያን ሲሆን በዕውቀታችን፤ በጉልበታችን፤ በገንዘባችንና በጊዜያችን ሁሉ እግዚአብሔርን ማገልገል ይጠበቅብናል፡፡አንዳንዶች ለምን አታገለግሉም ሲባሉ የማይረባ ምክንያት እየደረደሩ ከቤተ ክርስቲያን ይርቃሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ እንዲለመኑ፣ «እባካችሁ» እንዲባሉ ይፈልጋሉ፡፡ በማገልገላችን ከኃጢአት እንጠበቃለን፣ ሰላምና ተስፋ የተሞላበት ኑሮ እንኖራለን፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም «ስለዚህ ወንድሞቼ ሆይ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታፀኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉም» በማለት በአገልግሎት መትጋት እንደሚገባን ይመክረናል፡፡ (፩ኛጴጥ.፩፥፲)

ብዙዎች ከተመረቅን በኋላ አገልግሎት ያለ አይመሰለንም፡፡ አገልግሎታችንም ግቢ ጉባኤ ላይ ብቻ ይቀራል፡፡ ይህ ደግሞ የክርስትናውን ምሥጢር በአግባቡ አለማወቅ ነው፡፡ ጌታችንም ስለ ለቅዱሳን ሐዋርያት ስለ ነገረ ምጽአቱ ሲያስተምራቸው «እስከ መጨረሻው የሚጸና ግን እርሱ ይድናል» እንዳላቸው ግቢ ጉባኤ ብቻ በማገልገላችን የምንድን አይደለንም፤ እስከ መጨረሻው የሕይወት ፍጻሜ ድረስ ቃሉን በመጠበቅና በማገልገል መጓዝ እንጂ፡፡ (ማቴ.፳፬፥፲፫) የሕይወት አክሊልንም ለመቀበል እስከ መጨረሻው መትጋት ያስፈልጋል፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም  «ትቀበለው ዘንድ  ስላለህን መከራ ምንም አትፍራ፤ እነሆ እንድትፈተኑ ሰይጣን ከእናንተ አንዳንዶችን ወደ እሥር ቤት እንዲገቡ ያደርጋል፡፡  ዐሥር ቀንም መከራ ትቀበላላችሁ፤ እስከ ሞት ድረስም የታመንህ ሁን የሕይወት አክሊልንም እሰጥሃለሁ» ይላል፡፡ (ራዕ.፪፥፲)

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚገኙ መዋቅሮች ማለትም በሰ/ት/ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ በመታቀፍ ማገልገል ይገባል፡፡ በተለይም ለአገልግሎት   የሚመች ሰበካ ጉባኤ እንዲመሠረትና በዚያም ውስጥ የራስን አሻራ በማሳረፍ ቤተ ክርስቲያንን መደገፍ፣ የተሻለና ቀልጣፋ አሠራርን መከተል የሚያስችሉ መንገዶችን በመቀየስ የድርሻን መወጣት ያስፈልጋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በተመረቁበት የሙያ መስክ ገብተው አስፈላጊውን ሥራ መሥራት ብቻ በቂ አይደለም፡፡ በታማኝነትና በቅንነት መሥራትንም ይጠይቃል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ሁኔታ በአሁኑ ጊዜ የልጆቿችን ሙያ እንደምትሻ ግልጥ ነው፡፡ በተለይም የልማት ተቋማትን በማደራጅት (ለምሳሌ ፕሮጀክት በመቅረጽ) በኩል ያለባትን የመዋዕለ ንዋይ  ችግር ለመቅረፍ የምትወስዳቸው ርምጃዎች ማንነቷን የሚያሳውቁ እንጂ የሚያደበዝዙ እንዳይሆኑ  በውስጧ ሆነው ምሥጢሯንና  ቋንቋዋን የሚያውቁ የራሷ ልጆች ቢያጠኑላት ዛሬ የሚታዩት አስተዳደራዊ ችግሮች ባልተከሠቱ  ነበር፡፡

ተመርቀን ከየግቢ ጉባኤያት ተለይተን ወደ ሥራ ዓለም ስንሠማራ እንደ የአካባቢው ነባራዊ ሁኔታ በተለያዩ ደረጃዎች ላይ ያሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያጋጥሙናል፡፡ ተጠናክረው በጥሩ አገልግሎት የሚገኙ፣ ተቋቁመው በአገልጋይ እጥረት ምክንያት አገልግሎት ያቆሙ፣ እንዲሁም ያልተቋቋሙባቸው አካባቢዎች ሊያጋጥሙን ይችላል፡፡ ከጠንካሮቹ ሰ/ት/ቤቶች ልምድ በመውሰድ የሚጠናከሩበትን መንገድ ማሰብ፣ መቀየስና ተግባራዊ እንዲሆን የተቻለውን ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ በግቢ ጉባኤያት ካገኘናቸው ልምዶችም በመነሣት ስልት መቀየስ ከግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡

በየሄድንባቸው አካባቢዎች ሰ/ት/ ቤት ከማቋቋማችን በፊት አስቀድመን አካባቢውን ሕዝብ ጠባዩን ፍላጎቱን ባህሉንና የኗኗር ዘይቤውን ማጥናት ያስፈልጋል፡፡ ማጥናት፣ ከዚያም በቃለ ዓዋዲው መሠረት ማደራጀት እንዳለብን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ብዙ ከመናገር ብዙ መስማትና ከማገልገልም በፊት ብዙ መገልገልን መምረጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ያለውን ሁኔታ ሳናጠና በድፍረት መግባት መውጫችንን ያከብደዋልና፡፡ «እንደ እባብ ብልህ እንደ ርግብ የዋህ» መሆን ያስፈልጋል፡፡(ማቴ.፲፥፲፮) በተቻለ መጠን እኛ እንደ ወንድምና እኅት ቀርበን የሥጋዊ ሕይወታችን አለመሟላት መንፈሳዊና ሕይወታችንን እንደሚያጎድለው ብዙዎችም ወደ መጥፎ ሕይወት እንዳይገቡ ማሰገንዘብ አለብን፡፡

“ለፍጥረትም ሁሉ ወንጌልን ስበኩ” (ማር. ፲፮፥፲፭)

በእንዳለ ደምስስ

ይህንን ቃል ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሞቱ ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገለጠው በሌሊት ፈጥነው ወደ መቃብሩ ላመሩት ለመግደላዊት ማርያም እና እርሷን ተከትለው ለመጡት ሴቶች ነበር፡፡ ወደ መቃብሩም በደረሱ ጊዜ ሁለት መላእክት ተገልጠውላቸው መግደላዊት ማርያምን “አንቺ ሴት ምን ያስለቅስሻል?” አሏት፡፡ እርስዋም “ጌታዬን ከመቃብር ውስጥ ወስደውታል፤ ወዴትም እንደወሰዱት አላውቅም” አለቻቸው፡፡

ይህን ተናግራ ወደ ኋላዋ መለስ ስትል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቆሞ አየችው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም እንደሆነ አላወቀችም፡፡ … “አትንኪኝ፤ ወደ አባቴ አላረግሁምና ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሂጂና ወደ አባቴ ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬ ወደ አምላካችሁም አርጋለሁ አለ ብለሽ ንገሪያቸው” አላት፡፡

ማርያም መግደላዊት እና ሴቶቹም ፈጥነው ሄደው ሐዋርያት ተስፋ ቆርጠው በአንድነት ተሰብስበው እያዘኑና እያለቀሱ ሳሉ መግደላዊት ማርያም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መነሣት የምሥራች ነገረቻቸው፡፡ ነገር ግን አላመኗትም፤ ተረትም መሰላቸው፡፡ ሉቃስ እና ቀለዮጳም ተስፋ ቆርጠው ወደ ኤማሁስ ሲሄዱ እንደተገለጠላቸው ለሐዋርያቱ ምሥክርነት ቢሰጡም ሊያምኑ አልቻሉም፡፡ ከዚህ በኋላ ዐሥራ አንዱ ሐዋርያት በሐዘንና በትካዜ ውስጥ ሆነው ሳሉ ጌታችም መድኃኒታችን ኢሱስ ክርስቶስ በመካከላቸው ተገኝቶ ራሱን ገለጠላቸው፡፡

በመጨረሻም “ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፣ ለፍጥረትም ሁሉ ወንጌልን ስበኩ” በማለት ከተናገራቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ (ማር. ፲፮፥፲፭፤ ማቴ. ፳፰፥፩-፲፤ ሉቃ. ፳፬፥፩-፳፯)፡፡

ይህ ትእዛዝ ለሐዋርያት ብቻ ሳይሆን ከእነርሱ በኋላ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ለሚነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ መምህራንና ቃሉን ሰምተው አምነው ለሚያስተምሩ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዋስ ጠበቃ ለሆኑ ሁሉ ነው፡፡ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን ያመሰግኑ ዘንድ እንዲሁ ብርሃናችሁ በሰው ፊት ይብራ” ተብሎ እንደተጻፈ ጨለማውን ዓለም በወንጌል ብርሃንነት ተመርተው እንቅፋቱን ሁሉ ማስወገድ፣ እንደሚገባ ያስገነዝበናል፡፡ (ማቴ. ፭፥፲፬-፲፮)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ያሳድድ፣ ይገርፍና ያሠቃይ እንደነበር፤ ከዚያም አልፎ ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስን አይሁድ በድንጋይ ሲወግሩት የገራፊዎችን ልብስ እስከ መጠበቅ የደረሰ እንደ ነበር ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ ነገር ግን ያ ሁሉ አልፎ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ምርጥ ዕቃ” እስከ መሆን ደርሷል፡፡ “ተነሥና ሂድ፤ በአሕዛብና በነገሥታት በእስራኤል ልጆችም ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ አድርጌዋለሁና” እንዲል፡፡ ሳውል የተባለው ቅዱስ ጳውሎስም ወንጌል በዓለም ሁሉ ይዳረስ ዘንድ ሳይታክት እያስተማረና እየገሠጸ በአገልግሎቱ ጸንቶ ሰማዕትነትን እስኪቀበል ድረስ ለአምላኩ ታምኗል፡፡ (ሐዋ. ፯፥፶፬-፷፤ ፱፥፲፭)

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሆነን የእግዚአብሔር ማዕድ ከመደበኛው ትምህርት በተጨማሪ ተዘርግቶ ይጠብቀናል፡፡ በተመቻቸ ሁኔታ ውስጥ ሆነን ጊዜአችንን ብቻ መሥዋዕት በማድረግ የእግዚአብሔርን ቃል ለመማር የሚያቅተን ብዙዎች ነን፡፡ ለመማር ፈቃደኞች ሆነን ብንመጣም ከግቢ ተመርቀን ስንወጣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በክብር እንደተቀበለችን በክብር በአባቶች ቡራኬና መስቀል ባርካ ወደ ዓለም ስትልከን ስንቶቻችን እንሆን የተሰጠንን አደራ የምንወጣው?

ከግቢ ወጥተን ወደ ማኅበረሰቡ ስንቀላል ዓለም የራሷን ዝግጅት አድርጋ ትጠብቀናለች፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም “ልጆቼ ኑ፣ የሰጠኋችሁን አደራ ትወጡ ዘንድ ጊዜው ደርሷልና በደረሳችሁበት ሁሉ  መልካም የሆነውን አድርጉ” ትለናለች፡፡ የትኛውን ነው የምንመርጠው? እንደ ዴማስ መኮብለለን ወይስ እንደ ጢሞቴዎስ ታምኖ ማገልገል? ጢሞቴዎስ ወንጌሉን ከማን እንደተማረ ያውቃልና ለአምላኩም፣ ለመምህሩም ታምኖ ተገኘ፡፡ “አንተ ግን በተማርህበትና በተረዳህበት ነገር ጸንተህ ኑር፤ ከማን እንደተማርኸው ታወቃለህና፡፡” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ (፪ኛጢሞ.፫፥፲፬)

መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ፡- ዘሪ ዘሩን ሊዘራ ወጣ፤ አንዱም ዘር በመንገድ ላይ ወደቀና ተረገጠ፣ ሌላውም በጭንጫ መሬት ላይ ወደቀ፤ በበቀለም ጊዜ ወዲያው ደረቀ፤ ሌላውም በእሾህ መካከል ወደቀ፣ በአደገም ጊዜ እሾሁ አነቀውና ደረቀ፡፡ “በመልካም መሬት ላይ የወደቀ ዘርም ነበረ፡፡ በበቀለም ጊዜ መቶ እጥፍ አፈራ” ይለናል፡፡ በተሰማራንበት ሁሉ መሬት የተባለውን የሰዎችን ልብ አለምልመን ዘር የተባለውን የእግዚአብሔርን ቃል የምንዘራ የወንጌል ገበሬዎች ሆነን መገኘት ይጠበቅብናል፡፡ (ሉቃ. ፰፥፬-፰)፡፡

በግቢ ጉባኤያት ሳለን መንፈሳዊውን ዕውቀት ለመገብየት እንሮጥ እንደነበረው ሁሉ ዕውቀትን ከእምነት ጋር አዋሕደን ወደ ዓለም ስንሰማራ ከቀደመው ይልቅ መትጋት፣ ለገባነውም ቃል ታማኞች ሆነን መገኘት ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ሕይወታችንን በቃለ እግዚአብሔር በማነጽ በተሰማራንበት ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባሏት መዋቅሮች ውስጥ ገብተን ቃለ እግዚአብሔርን መማርና ማስተማርን የሥራችን አንድ አካል ልናደርግ ይገባል፡፡

ጌታችን በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ወንጌል “ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ያጠፋታል፤ ሰውነቱን ስለ እኔና ስለ ወንጌል የሚያጠፋትም ያገኛታል፡፡ ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ነፍሱን ግን ቢያጠፋ ለሰው ምን ይጠቅመዋል?” በማለት እንደገለጸው በተሰማራንበት ሁሉ ከፊታችን የሚያጋጥሙንን ፈተናዎች ሁሉ በመቋቋም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሰጠችን አደራ ታምነን ነፍሳችንን ማዳን፤ ለሌሎችም ብርሃን ሆነን የእግዚአብሔር መንግሥት ወራሾች እንሆን ዘንድ ዘወትር መትጋት ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ወብዙኃን ይትፌሥሑ በልደቱ፤ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” (ሉቃ. ፩፥፲፬)

መ/ር እንዳልካቸው ንዋይ

ይህን ቃል የተናገረው የእግዚአብሔር መልአክ ለካህኑ ዘካርያስ ነው፡፡ የጻፈልንም ከአራቱ ወንጌላውያን አንዱ የሆነው ቅዱስ ሉቃስ ነው፡፡ ይህ ቃል የተነገረለትም የካህኑ ዘካርያስና የኤልሳቤጥ ልጅ የሆነው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ነው፡፡ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አባቱ ዘካርያስ እናቱ ኤልሳቤጥ ይባላሉ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን እስኪወልዱ ድረስ በመካንነት (ያለ ልጅ) ኖረዋል፡፡

ጻድቃን መካን ሆነው የሚቆዩበት ጊዜ አለ፤ ኃጥአን መክነው የሚቀሩበት ሁኔታ አለ፡፡ እግዚአብሔር ባወቀ መክነው የሚቀሩም አሉ፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተገለጠው ምክነት (ልጅ መውለድ አለመቻል) በሦስት ዋና ዋና ምክንያቶች ሊመጣ ይችላል፡፡

. በኃጢአት፡

የሰው ልጅ ሕገ እግዚአብሔርን ሲተላለፍ፣ እግዚአብሔርን በሕይወቱ ማክበር ሲያቅተው፣ የቅዱሳንንም ክብር አልጠብቅ ሲል እግዚአብሔር ከቸርነቱ ብዛት የተነሣ ለሰው የሚሰጠውን ጸጋ ይነሳዋል፡፡ “ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታዎች ናቸው”ና፡፡ (መዝ.፻፳፯፥፫)  ልጅ ጸጋ ስጦታ ወይም ሀብት ነው፡፡ ጸጋ የሚሰጠው ደግሞ ለሚገባው ነው፡፡ ኃጢአት ደግሞ ጸጋን ያሳጣል፡፡ በኃጢአት ምክንያትም እግዚአብሔር ማሕፀናቸውን የዘጋባቸው እና ያለ ልጅ ያስቀራቸው ሰዎች አሉ፡፡ ከእነዚህም ሰዎች አንዷ የእስራኤል የመጀመሪያው ንጉሥ የሳዖል ልጅ እና በኋላም የነቢየ እግዚአብሔር የዳዊት ሚስት የሆነቸው ሜልኮል ናት፡፡

ዳዊት ታቦተ ጽዮን ከምርኮ በምትመለስበት ጊዜ ለታቦተ ጽዮን በዘመረ ጊዜ ሚስቱ ናቀችው፤ በዚህ ምክንያት እግዚአብሔር የሜልኮልን ማሕፀን ዘጋ፡፡ “ኢወለደት ሜልኮል እስከ አመ ሞተት፤ ሜልኮል እስከ ሞተችበት ቀን ድረስ ልጅ አልወለደችም፡፡” (፪ኛሳሙ. ፮፥፳፫) በማለት ይገልጻታል፡፡ በኃጢአት ከሚመጣው ምክነት ለመዳን ንስሓ መግባትና ወደ ፈሪሃ እግዚአብሔር መመለስ ይገባል፡፡

. ለሰዎች ጥቅም፡-

እግዚአብሔር የማይጠቅም ጸጋ አይሰጥም (፩ኛቆሮ. ፲፪፥፯) የቅዱሱ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት እናት እግዚእ ኃረያ እግዚአብሔርን ልጅ እንዲሰጣት በለመነችው ጊዜ አንድ ቃል ተናግራ ነበር፡፡ “የምትሰጠኝ ልጅ አንተን የሚፈራ የሚያገለግል ሰውን የሚያፍር ሃይማኖቱን የሚያከብር ይሁንልኝ ካልሆነ ግን ማህፀኔን ዝጋው” በማለት ነበር የተማጸነችው፡፡ (ገድለ ተ/ሃይማኖት፤ ገጽ ፳፰፤ ምዕ. ፰፥፶-፶፫) እግዚአብሔርም ጸሎቷን ሰምቶ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን የመሰለ ልጅ ሰጥቷታል፡፡ የማይጠቅም ልጅ ቢሆን ግን እግዚአብሔር አይሰጥም፡፡

. የሚወለደው ልጅ የተለየ ቅዱስ ከሆነ፡-

እግዚአብሔር ስለሚሰጠን ልዩ ስጦታ ብሎ ስጦታውን ሊያዘገየው ይችላል፤ ይህም የሚሆንበት ምክንያት ውድ ስጦታ ስለሆነ በደጅ ጥናት፣ በጸሎት፣ በሱባኤ እንዲሆን ሁለተኛም አክብረን እንድንይዘው ነው፡፡ በዚህ ምክንያት በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተነገረው ስለሚሰጣቸው በጎ ስጦታ በምክነት ያቆያቸው ቅዱሳን ሰዎች አሉ፡፡

ለምሳሌ፡-  ሣራ የአብርሃም ሚስት ለ፺ ዓመት ያህል በምክነት የቆየችው ይስሐቅን የመሰለ በጎ ስጦታ እግዚአብሔር ስላዘጋጀላት ነው፡፡ ሐና እና ኢያቄምም ያለ ልጅ የቆዩት የአምላክ እናት የምትሆን ድንግል ማርያምን ሊሰጣቸው ስለሆነ ነው፡፡ ዛሬም በዓለ ልደቱን የምናከብርለት ቅዱስ ዮሐንስ ወላጆቹ በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ የሚሄዱ ጻድቃን ሲሆኑ ያለ ልጅ በምክነት የቆዩት ክርስቶስን በዮርዳኖስ ባሕር ለማጥመቅ የሚበቃውን ደግ ሰው ስለሚወልዱ ነበር፡፡

ለዚህም ነበር መልአኩ የቅዱሱን ልደት አስመልክቶ “በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ሲል የተናገረው፡፡ ልደቱ ከእናትና አባቱ ጀምሮ የክርስቶስን መምጣት ለሚጠባበቁ ሁሉ ደስታ ነበር፤ ለዚህም ነው መልአኩ ስሙ ዮሐንስ ይባላል ያለው፡፡ ዮሐንስ ማለትም ፍስሓ ወሐሴት ፍቅር ወሰላም ማለት ነው፡፡ ከፅንሰቱ ጀምሮ እስከ ልደቱ በመላ ሕይወቱም ሁለንተናው በተአምር የተመላ ልጅ በማግኘታቸው ወላጆቹ ደስታን አግኝተዋል፡፡ ሲፀነስ የአባቱ አንደበት የመልአኩን ቃል ባለመቀበሉ ሲዘጋ ሲወለድ ደግሞ የአባቱን አንደበት ከፍቶ ቤቱን በደስታ የመላ ቅዱስ ሕፃን ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ዮሐንስን ልደት በየዓመቱ በታላቅ ክብር ታከብረዋለች፡፡

በዚህ አንጻር የእኛ ልደት እንዴት ነው እየተከበረ ያለው? በእኛ ልደት ቤተሰቦቻችን፣ ቤተ ክርስቲያንና ሀገራችን ምን ተጠቀሙ? በየዓመቱስ ልደታችን የምናከብርበት መንገድ ኦርቶዶክሳዊ የቅዱሳንን መንገድ የተከተለ ነው? የሚለውን ጥያቄ ራሳችንን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በልደቱ ብዙዎች ደስ ተሰኝተዋል፡፡ ምክንያቱም በትምህርቱ በተአምራቱ ብዙዎች ተጠቅመዋልና “የጌታን መንገድ አዘጋጁ” እያለ በትምህርቱ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ ያቀርብ ነበር፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በውኃ ለንስሓ በዮርዳኖስ ባሕር እያጠመቀ ለአማናዊ ጥምቀት ሰዎችን ያዘጋጅ ነበርና ብዙዎች በመወለዱ ተጠቅመዋል፡፡ እኛስ በመወለዳችን ማን ተጠቀመ? በቅዱስ ዮሐንስ መወለድ ግን ብዙ ድንቆች ሆነዋልና ደስ ይለናል፡፡ አስቀድመን እንዳነሣነው ስለ ክርስቶስ እያስተማረ፣ በበረሐ በመኖሩና ጌታን በማጥመቁ ቅድስናውን ማድነቅ፣ በቃል ኪዳኑም መጠቀም ከእኛ ይጠበቃል፡፡

ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ አለ።-

ሰባኬ ወንጌል በጥዑም ልሳኑ፣

ርስነ መለኮት ገሠሠት የማኑ፣

ፀጕረ ገመል ተከድነ ዘባኑ፣

ለዮሐንስ ሂሩቶ ንዜኑ ንዜኑ፡፡

ትርጉሙም

በጣፋጭ አንደበቱ ወንጌልን የሚሰብክ፤ የሚያቃጥል መለኮትን የዳሰሰች ቀን እጅ፤ ጀርባው በግመል ፀጕር የተሸፈነ የዮሐንስን ደግነት ፈጽመን እንናገራለን በማለት አመስግኖታል፡፡

በአጠቃላይ የዮሐንስ ልደት ለብዙዎች ደስታ ነው የተባለው ሰውን ሁሉ በንስሓ ወደ ጌታው የሚመልስ በመሆኑ ነው፡፡ ስለሆነም እኛም መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የጌታ መንገድ ጠራጊ ነውና በልደቱ ደስ ሊለን ይገባል፡፡

አምላከ ዮሐንስ ይርዳን፣ በበረከተ ልደቱም ይባርከን፡፡

“እነሆም ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካአል ሊረዳኝ መጣ” (ዳን. ፲፥፲፫)

ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ “መኑ ከመ አምላክ፤ ማን እንደ እግዚአብሔር” ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ወንጌላዊው ቅደስ ዮሐንስ በራእዩ “በእግዚአብሔር ፊት የቆሙ ሰባት መላእክትን አየሁ” ብሎ ከተናገረላቸው መላእክት ውስጥ አንዱ ሲሆን፤ የሰባቱም ሊቃነ መላእክት አለቃ እንዲሆን እግዚአብሔር መርጦ ሹሞታል፡፡

እስራኤላውያን ለ፪፻፲፭ ዓመታት በግብፃውያን ከደረሰባቸው የባርነትና የሥቃይ ዘመናት በኋላ በሊቀ ነቢያት ሙሴ አማካይነት ወደ ምድረ ርስት ሲወጡ ቀን በደመና፣ ሌሊቱን በብርሃን እየመራ ማድረሱን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በማለት ይነግረናል፡- “በመንገድ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀሁልህም ስፍራ ያገባህ ዘንድ እነሆ፥ እኔ መልአኬን በፊትህ እልካለሁ። ራስህን ጠብቅ፣ ስማው፣ እምቢም አትበለው፤ ስሜም በእርሱ ስለሆነ ይቅር አይልምና፡፡” (ዘጸ. ፳፫፥፳-፳፩) እንዲል፡፡

ቅዱስ ሚካኤል ከግብሩ በመነሣት በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ በልዩ ልዩ ቅጽል ስያሜዎች ይጠራል፡፡ ከእነዚህም መካከል “መጋቤ ብሉይ፣ መልአከ ኃይል፣ እንዲሁም መልአከ ምክር” ይባላል፡፡ መጋቤ ብሉይ መባሉ በብሉይ ኪዳን ከእግዚአብሔር እየተላከ እስራኤላያንን ቀን በደመና፣ ሌሊቱን በብርሃን እየመራ መና ከሰማይ እያወረደ በመመገቡ፣ መልአከ ኃይል መባሉም እግዚአብሔር በእርሱ አማካይነት ታላላቅ ሥራዎችን በመሥራት ኃይሉን የገለጸ፣ ዲያብሎስን ከነሠራዊቱ ድል ያደረገ በመሆኑ ሲሆን፣ መልአከ ምክር ወይም የእግዚአብሔር የምክሩ አበጋዝ የተባለበት ምክንያት እግዚአብሔርን በምክሩ ይረዳዋል ለማለት ሳይሆን እግዚአብሔር የሚሠራውን ሥራ ለወዳጁ ለቅዱስ ሚካኤል ይገልጽለታል፤ በእርሱም አማካኝነት ይሠራል ለማለት ነው፡፡

የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በስሙ ለሚማጸኑ ሁሉ ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ከሚደርስባቸው ችግር ሁሉ የሚታደግ መልአከ ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት ቅዱስ ሚካኤል ያደረጋቸውን ቁጥር ስፍር የሌላቸው ተአምራት ቢኖሩም በተለይም በሰኔ ፲፪ ቀን ያደረገውን ተአምራት ከብዙ በጥቂቱ እንደሚከተለው በአጭሩ እንመለከታለን፡፡

በእስክንድርያ ሀገር አክላወባጥራ የተባለች ንግሥት የንጉሥ በጥሊሞስ ልጅ ዙሐል በሚባል ኮከብ ስም ያሠራችው ታላቅ ምኵራብ ነበረና በየዓመቱ ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን በዚያ ምኵራብ ሕዝቡ ተሰብስቦ ታላቅ በዓል ያደርጉ ነበር፡፡ በዚያም ምኵራብ ውስጥ ዙሐል የሚሉት ታላቅ የነሐስ ጣዖት ነበረና በዓሉ በሚከበርበት ዕለት ብዙ ፍሪዳዎችን ያርዱለት ነበር፡፡ ሊቀ ጳጳሱ እለእስክንድሮስ እስከተሾመበት ዘመን ድረስ ለዚያ ጣዖት እንዲህ ሲያደርጉ ኖሩ፡፡

እለእስክንድሮስ በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ እና ቆስጠንጢኖስም በነገሠ ጊዜ የክርስትና ሃይማኖት ስለ ተስፋፋች ያን ጣዖት አባ እለእስክንድሮስ ሊሠብረው ወደደ፡፡ ነገር ግን የሀገሩ ሰዎች “እኛ በዚህ ቦታ ይህን በዓል ማክበርን ለምደናል፡፡ እነሆ ከአንተ በፊት ዐሥራ ስምንት ሊቃነ ጳጳሳት አልፈዋል፤ ይህን ልማዳችንንም አልለወጡብንም” በማለት ተከራከሩት፡፡ አባ እለእስክንድሮስ ግን ገሠፃቸው፤ አስተማራቸውም፡፡

“ይህ ጣዖት የማይጎዳና የማይጠቅም ነው፡፡ እርሱንም የሚያመልክ ሰይጣናትን ያመልካቸዋል፡፡ምክሬንስ ብትሰሙ ቀድሞ እንደ ነበረ አድርጌ ይህን በዓል እሠራላችኋለሁ፤ ይኸውም ጣዖቱን እንድንሰብረው፣ ምኵራቡንም እንድንባርከውና በከበረ መልአክ በመላእክት አለቃ በሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አድርገን እንድንሰይመው ነው፡፡ እኛም ይህን ታላቅ በዓል እንሠራለን፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነት ያለው ስለ ኾነ ስለ እኛ ይማልዳልና፡፡” ይህንንም ብሎ በዚህ በጎ ምክር አስወደዳቸው፤ እነርሱም ታዘዙለት፡፡

ከዚህም በኋላ ያንን ምኵራብ አድሰው በዚህ የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አደረጉት፡፡ በዚችም ዕለት አከበሩዋት፡፡

እግዚአብሔርን የሚፈራ የከበረ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለተኛው ቀን ይልቁንም በሰኔ እና በኅዳር ወር አብልጦ የሚያከብር አንድ ሰው ነበር፡፡ በጐረቤቱም ርኅራኄ የሌለው አንድ ባለ ጠጋ ሰው ነበረ፡፡ ይህን እግዚአብሔርን የሚፈራውን ሰው የከበረ መልአክ የሚካኤልን በዓል በሚያደርግበት ጊዜ ይጠላውና ያቃልለው ነበር፡፡ ከኃላፊው ዓለም ድካምም የሚያርፍበት ጊዜ በደረሰ ጊዜ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ታደርግ ዘንድ ሚስቱን አዘዛት፡፡ ከዚህም በኋላ ዐረፈ፡፡

ሚስቱም ፀንሳ ነበር፡፡ የመውለጃዋ ደርሶ ምጥ በያዛት ጊዜም በታላቅ ጭንቀት ውስጥ ሆና ጸለየች፡-የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ሚካኤልን በአማለጅነቱ ይደርስላት ዘንድ ተማጸነቸው፡፡ በዚህ ጊዜ በቤቷ ውስጥ ብርሃን በራ፡፡ መልኩ ውብ የኾነ ወንድ ልጅንም ወለደች፡፡ የእግዚአብሔርም መልእክተኛ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ሕፃኑን እንዲህ ብሎ ባረከው፡- “ርኅራኄ የሌለውን የዚህን ባለጠጋ ገንዘብና ሀብት፣ ጥሪቱንም ዅሉ ይህ ሕፃን እንዲወርስ እግዚአብሔር አዝዟል” አለ፡፡

ባለ ጠጋውም በቤቱ፣ በዐልጋው ላይ ሳለ ጌታ ጆሮውን ከፍቶለት ይህን ነገር ከመልአኩ ሰማ፡፡ ይህንን በሰማ ጊዜ ታላቅ ኀዘን ደረሰበት፡፡ ሕፃኑንም የሚገድልበትን ምክንያት ይፈልግ ጀመረ፡፡   ምክንያትም አዘጋጅቶ “የሚያገለግለኝ ልጅ ይኾነኝ ዘንድ ልጅሽን ስጪኝ፡፡ እኔም እየመገብኹና እያለበስኹ አሳድገዋለሁ፡፡ ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለሁ” አላት፡፡ ይህንንም ነገር ከባለጠጋው በሰማች ጊዜ ስለ ችግሯ እጅግ ደስ አላት፡፡ ልጅዋንም ሰጠችው፡፡

ባለጠጋውም በልጁ ቁመት ልክ ሣጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሣጥኑ ውስጥ አስገብቶ ከዘጋበት በኋላ   ወስደው በባሕር ጣሉት፡፡ ለሃያ አንድ ቀናትም ሳጥኑ በባሕሩ ላይ እየተንሳፈፈ ወደ አንድ ወደብ ደረሰ፡፡ በዚያም በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ሣጥኑን በውኃ ላይ ተንሳፎ አየው፡፡ እርሱም ከባሕሩ አውጥቶ ወደ ቤቱ ወሰደው፡፡ ሳጥኑ በቁልፍ የተቆለፈ ስለነበር ለመክፈት ተቸገረ፡፡ ነገር ግን አንድ አሣ የሚያጠምድ ሰው በማግኘቱ “መረብህን በኔ ስም ጣል፡፡ ለሚያዘው ዓሣ ዋጋውን እሰጥሃለሁ አለው፡፡

አጥማጁም እንዳለው አደረገ፡፡ ያን ጊዜም ታላቅ ዓሣ ተያዘ፡፡ ይዞም ወደ ቤቱ ሔደ፡፡ ለራትም ይጠብሰው ዘንድ አረደው፡፡ በሆዱም ውስጥ መክፈቻ አገኘ፡፡ በሣጥኑ ቀዳዳም በአስገባው ጊዜ ፈጥኖ ተከፈተ፡፡ በውስጡም ታናሽ ብላቴና አገኘ፡፡ ልጅ የለውም ነበርና ታላቅ ደስታ ደስ አለው፡፡ ጌታችንንም አመሰገነው፡፡ ሕፃኑንም በመልካም አስተዳደግ አሳደገው፡፡ ሕፃኑም አድጎ ጐልማሳ ኾነ፡፡

ከብዙ ዘመናትም በኋላ ያ ባለ ጠጋ ተነሥቶ ወደዚያ አገር ሔደ፡፡ በመሸም ጊዜ ወደ በግ ጠባቂው ደጅ ደረሰ፡፡ በግ ጠባቂውን “እስከ ነገ የምናድርበት ማደሪያ በአንተ ዘንድ እናገኛለን?  ኪራዩንም እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ባለ ጠጋውም በዚያ አደረ፡፡ ራት በሚቀርብም ጊዜ ከባሕር ላገኘው ልጅ “ባሕራን” ብሎ ሲጠራው ባለ ጠጋውም ሰምቶ “ልጅህ ነውን?” ብሎ ጠየቀው፡፡ በግ ጠባቂውም “አዎ፤ ታናሽ ሕፃን ኾኖ ሳለ ከሃያ ዓመት በፊት ከባሕር ላይ አግኝቼዋለሁና እግዚአብሔር የሰጠኝ ልጄ ነው” አለው፡፡

ባለጠጋውም እርሱ ወደ ባሕር የጣለው ሕፃን መኾኑን ዐውቆ እጅግ አዘነ፡፡ በማግሥቱም ጎዳናውን ሊጓዝ በተነሣ ጊዜ ሰይጣናዊ ምክንያት አመካኝቶ በግ ጠባቂውን እንዲህ አለው፡- “ከአገር ስወጣ በቤቴ የረሳሁት ጉዳይ ስላለ እንድልከው ልጅህን ትሰጠኝ ዘንድ እሻለሁ፡፡ እኔም የድካም  ዋጋውን ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሃለሁ” አለው፡፡

የብላቴናውም አባት ስለ ገንዘቡ ደስ ብሎት ልጁ ባሕራንን ሰጠው፡፡ ባለ ጠጋው ወደ መጋቢው ደብዳቤ ጻፈ፤ “ይቺን ደብዳቤ በምታነባት ጊዜ ደብዳቤዋን ይዞ የመጣውን ልጅ ገድለህ በጉድጓድ ውስጥ ጣለው፤ ማንም ዐይወቅ፡፡” በማለት በመካከላቸውም የሚተዋወቁበትን ምልክት ጽፎ አሸጋት፤ ለባሕራንም ሰጠው፡፡

ባሕራንም ሲጓዝም ሰንብቶ የአንዲት ቀን ጉዞ ሲቀረው እነሆ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በንጉሥ ጭፍራ አምሳል በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ “አንተ ጐልማሳ የያዝኸው ምንድነው?” አለው፡፡ “ከአንድ ባለጠጋ የተጻፈች መልእክት ናት” አለው፡፡ “ያቺን ደብዳቤ አሳየኝ አለው፡፡ እርሱም ስለ ፈራ ሰጠው፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ያቺን የሞት መልእክት ደመሰሳት፡፡ በእርሷ ፈንታም በንፍሐት ለውጦ እንደህ ብሎ ጻፈ፤ “ይቺን ደብዳቤ ይዞ ለመጣ ባሕራን ለሚባል ሰው ልጄን አጋቡት፡፡ በውስጥና በውጭ ያለ ንብረቴንና ጥሪቴን፣ ወንዶችና ሴቶች ባሮቼን፣ ጠቅላላ ንብረቴንም አውርሼዋለሁና የፈለገውንም ሊያደርግ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና እኔን አትጠብቁኝ፡፡ እኔ ብዙ እዘገያለሁ ለዚህም በእኔና በአንተ መካከል ይቺ ምልክት እነኋት፡፡” በማለት ደብዳቤውን አሽጐ ለባሕራን ሰጠው፡፡ “ወደ ባለጠጋው ቤት ሒደህ ይቺን ደብዳቤ ለሹሙ ስጠው፡፡በጎዳናም እኔ እንደ ተገናኘሁህ    አትንገረው፡፡ እንዳይገድልህም ይህን የሞት ደብዳቤ ለውጬልሃለሁ” አለው፡፡ ባሕራንም “እሺ ጌታዬ ያዘዝኸኝን ዅሉ አደርጋለሁ” አለ፡፡

ባሕራንም ወደ ባለ ጠጋው ቤት በደረሰ ጊዜ ያቺን ደብዳቤ ለሹሙ ሰጠው፡፡ በአነበባት ጊዜ በመካከላቸው ያለውን ምልክት አገኘ፡፡ አስተውሎም እርግጠኛ እንደ ኾነ ዐወቀ፡፡ ከዚህም በኋላ ለባሕራን ሠርግ አዘጋጅቶ እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል የባለ ጠጋውን ልጅ አጋቡት፡፡ ዐርባ ቀን ያህልም ደስታና ሐሴት እያደረጉ ኖሩ፡፡ ከዚህ በኋላ ባለ ጠጋው ከሔደበት መመለሻው ጊዜ ኾኖ በደስታ የኾነውን የመሰንቆና የእንዚራ ድምፅ ሰምቶ “ይህ የምሰማው ምንድነው”  ብሎ ጠየቀ፡፡ እነርሱም “ስሙ ባሕራን ለተባለ የአንተን ደብዳቤ ላመጣ ጐልማሳ ሰው ልጅህ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ እነሆ ለዐርባ ቀናት በሠርግ ላይ ነው፡፡ገንዘብህንና ጥሪትህን ዅሉ ወንዶችና ሴቶች ባሮችህን አንተ እንዳዘዝኽ ሰጥተውታል” አሉት፡፡ ይህንም በሰማ ጊዜ ደንግጦ ከፈረሱ ላይ ወደቀ በድንገትም ሞተ፡፡

ባሕራንም በጎ ሥራዎችን የሚሠራ ኾነ፡፡ የተገለጠለትና ከመገደል ያዳነው የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል እንደ ኾነ፤ ሊገድለው የሚሻውን የባለ ጠጋውን ጥሪቱን ዅሉ ያወረሰውም እርሱ እንደ ኾነ ተረዳ፡፡ የዚህንም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን መታሰቢያ በየወሩ ያደርግ ጀመረ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠራለት፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕሉን አሥሎ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ አደረገው፡፡ ከእርሱም ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡

ዳግመኛም በዚህች ቀን እግዚአብሔርን የሚፈራ አስተራኒቆስ የሚስቱ የቅድስት አፎምያ የዕረፍቷ መታሰቢያ ኾነ፡፡ ይህም ሰው በየወሩ ሦስት በዓላቶችን እያከበረ ኖረ፡፡ እሊህም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ በየወሩ በሃያ ዘጠኝ፤ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓል መታሰቢያ በየወሩ በሃያ አንድ፤ የከበረ የመላእክት አለቃ የኾነ የቅዱስ ሚካኤል በዓል መታሰቢያም በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን ናቸው፡፡ የሚሞትበትም ጊዜው ሲቀርብ እርሱ ሲሠራው የነበረውን ምጽዋት ይልቁንም እሊህን ሦስቱን በዓላት እንዳታስታጉል ሚስቱን ቅድስት አፎምያን አዘዛት፡፡

እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባሏን ለመነችው፡፡ እርሱም አሠርቶ ሰጣትና በቤቷ ውስጥ በክብር አኖረችው፡፡ ባሏም ከዐረፈ በኋላ ባሏ ያዘዛትን መሥራት ጀመረ፡፡ ሰይጣን ግን ቀናባት፡፡ በመበለት ሴት መነኵሲት ተመስሎ ከእርሷ ጋር ተነጋገረ፡፡ እንዲህም አላት፤ “እኔ አዝንልሻለሁ፤ እራራልሻለሁም፡፡ ገንዘብሽ ሳያልቅ፣ የልጅነትሽም ወራት ሳያልፍ አግብተሽ ልጅ ትወልጂ ዘንድ እመክርሻለሁ፡፡ባልሽም መንግሥተ ሰማያትን ወርሷል፡፡ ምጽዋትም አይሻም፡፡” አፎምያም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ “እኔ ከሌላ ሰው ጋራ ላልገናኝ በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን አድርጌያለሁ፡፡ ርግቦችና መንጢጦች እንኳ ሌላ ባል አያውቁም፡፡ በእግዚአብሔር አርአያ ከተፈጠሩ ሰዎች ይህሊኾን እንዴት ይገባል?”

ምክሩንም ባልሰማች ጊዜ አርአያውን ለውጦ በላይዋ ጮኸባት፡፡ እንዲህም አላት፤ “እኔ በሌላ ጊዜ እመጣለሁ፡፡” እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ይዛ አሳደደችው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን የከበረ የመልአኩ የሚካኤል በዓል በሚከብርበት ዕለት እርሷም የበዓሉን ዝግጅት ስታዘጋጅ ሳለች ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ “አፎምያ ሆይ! ሰላም ላንቺ ይኹን! እኔ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ነኝ፡፡ ጌታ ወደ አንቺ ልኮኛልና እርሱም ይህን መመጽወትሽን ትተሽ ለአንድ ምእመን ሚስት ትኾኚ ዘንድ አዞሻል፡፡” ባል የሌላት ሴት መልሕቅ የሌለውን መርከብ እንደምትመስል ዕወቂ፤ እንደ አብርሃምና ያዕቆብ እንደ ዳዊትም እንደነርሱ ያሉ ብዙ ሴቶችን እንዳገባ፤ እግዚአብሔርንም ደስ እንዳሰኙት ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጥቅሶችን ያመጣላት ጀመረ፡፡

ቅድስትአፎምያም መልሳ “አንተ የእግዚአብሔር መልአክ ከኾንኽ የመስቀል ምልክት ከአንተ ጋር ወዴት አለ? የንጉሥ ጭፍራ የኾነ ዅሉ የንጉሡን ማኅተም ሳይዝ ወደ ሌላ ቦታ አይሔድምና” አለችው፡፡ ሰይጣኑም ይህንን በሰማ ጊዜ መልኩ ተለወጠና አነቃት፡፡ እርሷም ወደ ከበረው መልአክ ወደ ሚካኤል ጮኸች፡፡ ወዲያውኑም ደርሶ አዳናት፡፡ ያንም ሰይጣን ይዞ ይቀጣው ጀመረ፡፡ ሰይጣኑም ጮኸ፡፡ “ማረኝ፤ ያለ ጊዜዬ አታጥፋኝ፤ እግዚአብሔር እስከ ዓለም ፍጻሜ ታግሦናልና” እያለ ለመነው፡፡ ከዚያም ተወውና አባረረው፡፡

የከበረ መልአክ ሚካኤልም እንዲህ አላት፤ “ብፅዕት አፎምያ ሆይ! ሒደሽ የቤትሽን ሥራ አዘጋጂ፡፡አንቺ ዛሬ ከዚህ ዓለም በሞት ትለዪአለሸና፡፡ እነሆ እግዚአብሔርም ዐይን ያላየውን፣ ጆሮም ያልሰማውን፣ በሰው ልብም ያልታሰበውን አዘጋጅቶልሻል፡፡” ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጣት፡፡ ወደ ሰማያትም ዐረገ፡፡ የበዓሉንም ዝግጅት እንደሚገባ ከፈጸመች በኋለ ወደ ኤጲስቆጶሱና ወደ ካህናቱ ዅሉ ላከች፡፡ ወደ እርሷም በመጡ ጊዜ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ይሰጧቸው ዘንድ ገንዘቧን ዅሉ አስረከበቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ተነሥታ ጸለየች፡፡ የከበረ የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤልንም ሥዕል አንሥታ ታቅፋ ሳመችው፡፡ ያን ጊዜም በሰላም ዐረፈች፡፡

ስለዚህም የዚህን ታላቅ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ለማድረግመታገል ይገባናል፡፡ “እነሆም ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካአል ሊረዳኝ መጣ” (ዳን. ፲፥፲፫) እንዲል ቅዱስ ሚካኤል በምልጃው ይራዳን ዘንድ ልንማጸነው ይገባል፡፡ እርሱ ከሰይጣን ወጥመድ ያድነን ዘንድ በዘመናችን ዅሉም ይጠብቀን ዘንድ፤ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይ ዘንድ፤ መከራችንንም ያርቅ ዘንድ፤ የምድራችንንም ፍሬ ይባርክ ዘንድ፤ ፈቃዱንም ለመሥራት ይረዳን ዘንድ፤ ከእኛ ወገን የሞቱትን ዕረፍተ ነፍስ ይሰጥ ዘንድ፤ ወደ መንገድ የሔዱ አባቶቻችንና ወንድሞቻተንን ወደ ቤቶቻቸው በሰላም፣ በጤና ይመልሳቸው ዘንድ፤ በመካከላችንም ፍቅር ያደርግልን ዘንድ፤ እስከ መጨረሻዪቱም ሕቅታ ድረስ በቀናች ሃይማኖት ያጸናን ዘንድ፤ የክርስቶስ ወገኖች የኾኑ መኳንንቶቻችንንም ጠብቆ በወንበሮቻቸው ላይ ያጸናቸው ዘንድ፤ የሳቱትንም ወደ ቀናች ሃይማኖቱ ይመልሳቸው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ ይለምናልና፡፡

የቅዱስ ሚካኤል አማላጅነትና ጥበቃው አይለየን፡፡ አሜን፡፡

 

ምንጭ፡– መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፲፪ ቀን፡፡

“እየባረካቸው ራቃቸው” (ሉቃ. ፳፬፥፶፩)

ዘመነ ዕርገት ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በኋላ ከ፵ኛው ቀን ጀምሮ እስከ ጰራቅሊጦስ ድረስ ያለው ነው፡፡ ዕርገት ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከ፱ኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ነው፡፡ የጌታችን ዕርገት ታሪክ በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፬፥፶ ጀምሮ የተጻፈ ሲሆን ደቀ መዛሙርቱ በዓይናቸው እያዩት፣ እየባረካቸው ከዓይናቸው መሠወሩ ተገልጧል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገቱን ለሐዋርያት ማሳየቱ ለቅዱሳን፣ ጻድቃን ዕርገት እንዳላቸው ለማሳየት ነው፡፡ እርሱ ሰው ሲሆን ያየው የለም፤ሲያርግ ግን ሁሉ እያየው ነው፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ፴፫ ዓመት ከሦስት ወር እየተመላለሰ ክርስትናን ሰብኳል፣ ድውያንን ፈውሷል፤ ከተነሣ በኋላም ለ፵ ቀናትም ለሐዋርያት እየተገለጠ ጸሎተ ኪዳንን አስተምሮ ዐርጓል፡፡

ይህም ማለት ፶፻ወ፭፻ (አምስት ሺህ አምስት መቶ) ዘመን ሲፈጸም በዘመነ ማቴዎስ ማክሰኞ መንፈቀ ሌሊት ተወልዶ በዘመነ ማርቆስ በዕለተ ሐሙስ በ፫ ሰዓት ግንቦት ፰ ቀን ዐረገ፡፡

ጌታችን ከትንሣኤ በኋላ ዐርባ ቀን ሐዋርያትን እያስተማረ ስለሚመጣው አጽናኝ እያስረዳ ሰነበተ (ዮሐ. ፳፩፥፫) ቅዱስ ዳዊትም “እግዚአብሔር  በመለከት ድምፅ  ዐረገ ዘምሩ ለአምላካችን ዘምሩ ለንጉሣችን ዘምሩ፣ እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና በማስተዋል ዘምሩ”   ይላል (መዝ.፵፮፥፭—፯)

ሠለስቱ ምዕትም “ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ፤ በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ” ብለዋል፡፡ (ጸሎተ ሃይማኖት) “እንግዲህ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን ሹ በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም ሞታችኋልና ሕይወታችሁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሮአልና፡፡ ሕይወታችሁም የሆነ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ በዚያን ጊዜ እናንተ ደግሞ   ከእርሱ ጋር ትገለጣላችሁ” እንዲል፡፡ (ቆላ. መ፫፥፩-፬)

የዕርገት በረከቶች

. ቡራኬ፡- “እጆቹን በላያቸው ላይ ጭኖ ባረካቸው፣እየባረካቸውም ራቃቸው ወደ ሰማይም ዐረገ” ይላል፡፡ (ሉቃ. ፳፬፥፶፩) ይህ ቡራኬ ለቅዱሳን ሐዋርያት በመዋዕለ ሥጋዌው ከሆነው የመጨረሻ ቡራኬ ነው፡፡ ይህን ቡራኬ ለመቀበል መጽናትና መታገስ ይጠይቃል፡፡ በክርስቶስ ትምህርት የጸኑት የተባረኩበት ነው፡፡ቡራኬው ዛሬም የማይቋረጥ መሆኑን ሲያረጋግጥልን ደግሞ “እየባረካቸው ራቃቸው፣ ወደ ሰማይም ወጣ” በማለት ይነግረናል፡፡

ዛሬም ቤተ ክርስቲያናችን በቅዳሴ ፍጻሜ ላይ ካህኑ እጆቹን አመሳቅሎ “እግዚአብሔር ከሁላችሁ ጋር ይሁን” በማለት የዕርገት በረከት (ቡራኬ) ለምእመናን ስታድለው(ስታካፍለው) ትኖራለች፡፡ ይህ ደግሞ “እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” (ማቴ. ፳፰፥፳) በማለት የገባልን ኪዳን ማረጋገጫ ቡራኬ ነው፡፡

፪. ሹመት፡- “ወእምዝ አውፅኦሙ አፍአ እስከ ቢታንያ ወአንሥአ እዴሁ ላዕሌሆሙ ወባረኮሙ፤ ወደ አፍአ እስከ ቢታንያ ድረስ አውጥቶ በአንብሮተ እድ እስከ ፖትርያርክነት ያለውን ማዕርግ ሾማቸው፤ ሾሟቸውም የርቀት ያይደለ የርኅቀት ተሰውሯቸው ወደ ሰማይ ዐረገ” (የሉቃስ ወንጌል አንድምታ ምዕራፍ ፳፬፥፶-፶፩)፡፡ በቅዱሳን ሐዋርያት እስከ ዕርገት ድረስ የተሰጣቸው ሹመት ሁሉ በቡራኬ የተረጋገጠው በዕርገት ዕለት ነው፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሥልጣን ሰጣቸው የሚለውን ሲያብራሩ አስቀድሞ የሰጣቸውን ለማጽናት ነው ብለው ያስተምራሉ፡፡

. ተስፋ፡-  መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት እንደሚወርድላቸው ተጽፏል፡፡ (ዮሐ. ፲፭፥፳፮፣ ሉቃ. ፳፬፥፵፱) ዳግመኛም ሐዋርያትን “እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ” (ዮሐ. ፲፬፥፫) በማለት የሰጠን የመጨረሻ ተስፋ የተረጋገጠበት ነው፡፡

“…. ወደሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት እንዲሁ ይመጣል” (የሐዋ. ፩፥፲፩) በማለት አስረግጠው ቅዱሳን መላእክት ተናግረዋል፡፡ አቡቀለምሲስ ዮሐንስም “እነሆ ከደመና ጋር ይመጣል፣ ዐይንም ሁሉ የወጉትም ያዩታል” (የዮሐንስ ራዕይ ፩፥፯) በማለት በዕርገቱ ያየነውን ደመና በዳግም ምጽአቱ እንደምናየው አስተምሮናል፡፡

                 ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ይህን ያውቃሉ?

  • የመጀመሪያውየግቢ ጉባኤያት ተወካዮች ሀገር ዐቀፍ ሴሚናር ከየካቲት ፲፫-፲፬ ቀን በ፲፱፺፩ ዓ.ም ተከናወነ፡፡
  • በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤት ሲማሩ የቆዩ የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የመጀመሪዋ  የደረቅ ቅጅ /Hard copy/ የምረቃ መጽሔት በ፲፱፻፹፮  ዓ.ም ተዘጋጀ፡፡
  • የመጀመሪያዋ ጉባኤ ቃና ጋዜጣ ቁጥር ፩ የካቲት ፳፻ ዓ.ም መታተሟና ዋጋዋም  ፩ ብር ከ፳፭ ሣንቲም የነበረ ሲሆን የገጽ ብዛቱም ፰  ነበር፡፡
  • ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ውስጥ ፬፻፳፱ እና ፳፫ በውጭ ሀገራት ግቢ ጉባኤያትን እያስተማረ  ይገኛል፡፡
  • በሀገር ወስጥ ፪፻፹፮፣ በውጭ ሀገራት ፲፯ የጸደቁ ግቢ ጉባኤያት እና በሀገር ውስጥ ፻፵፭ በክትትል ላይ  ያሉ፣  በውጭ  ሀገራት ደግሞ ፮ ግቢ ጉባኤያት ይገኛሉ፡፡
  • ማኀበረ ቅዱሳን በአጠቃላይ ፬፻፶፬(፬፻፴፩ በሀገር ውስጥ እና ፳፫ በውጭ ሀገራት) ግቢ ጉባኤያትን  እያስተማረ መሆኑን ያውቃሉ?
  • የመጀመሪያው የግቢ ጉባኤያት የተከታታይ ትምህርት /course/ ማስተማሪያ መጻሕፍት ዝግጀት የተጀመረው በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ነበር፡፡ በተቀረጸው ሥርዓተ ትምህርት /carricullum/ ውስጥ ፳፪ የተከታታይ ትምህርት መጻሕፍትን በማዘጋጀት የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን ነገረ ሃይማኖት ማስተማሩን ቀጠለ፡፡
  • በ፳፻፭ ዓ.ም የሥርዓተ ትምህርት ክለሳ በማድረግ የትምህርት ዓይነቶቹን ወደ ፲፩ ዝቅ በማድረግ እስከ አሁን  በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ለሚማሩ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች  በማስተማር ላይ ይገኛል፡፡
  • ከ፳፻፲፩ ዓ.ም ባሉት ዓመታት የምረቃ መጽሔትን ከወረቀት ኀትመት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ወደሚታገዝ (Digital) አሠራር እንዲቀየር ስምምነት መደረሱን እና ከ፳፻፲፪ ዓ..ም ጀምሮ ሙሉ በሙሉ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ወደሚታገዝ (Digital) አሠራር ተቀየረ፡፡
  • ማኅበሩ በ፲፱፻፺፩ ዓ.ም በክረምቱ ወራት ለተተኪ መምህራን በአማርኛ ሥልጠና መስጠት ሲጀምር፣ ከ፲፱፻፺፯ ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ በአፋን ኦሮሞ መስጠት ቀጠለ፡፡ በአሁኑ ወቅት በአፋን ኦሮሞ ማስተማር የሚችሉ መምህራንን ማፍራት ችሏል፡፡
  • ማኅበረ ቅዱሳን ከየካቲት ፳፻ ዓ.ም ጀምሮ በተለይ ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች “ጉባኤ ቃና” የተሰኘ መጽሔት በየ፫ ወሩ በአማርኛ እንዲሁም በአማርኛ የተዘጋጀው መጽሔት ወደ አፋን ኦሮሞ በመተርጎም አዘጋጅቶ ማሠራጨት ጀመረ፡፡
  • ማኅበሩ ምንም እንኳን የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት አስተምሮ በአባቶች ቡራኬ የሚያስመርቃቸው ኦርቶዶክሳውያን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ከመላው ሀገሪቱ የተውጣጡ፣ ከ፹ በላይ የሚሆኑ ቋንቋዎችን የሚናገሩ ቢሆኑም ከኦሮምያ ክልል የሚመጡት በሃይማኖታቸው እንዲጸኑና ከተለያዩ አካላት የሚደረግባቸውን ጫና መቋቋም እንዲችሉ በማሰብ ለሁሉም የሚታተመው የምረቃ መጽሔት በልዩ ሁኔታ በአፋን ኦሮሞ ጭምር ተተርጉሞ እንዲታተም እየተደረገ መሆኑን ያውቃሉ?

“የሕይወት ቀን” በግቢ ጉባኤያት

ወርቃማው የወጣትነት ዘመናችን በተስፋ፣ በመልካም ምኞትና በትጋት የተሞላ፣ ዕውቀትንና አቅምን ያማከለ ማንነታችን የሚታነጽበት፣ መንፈሳዊነታችን የሚገለጽበት የዕድሜ ክልል እንደመሆኑ የሕይወታችን መሠረት ነው፡፡ መንፈሳዊ ፍሬን አፍርተን ርስተ መንግሥተ ሰማያት ለምንወርስብትም የሕይወት ስንቅ የምንሰንቅበት የተጋድሎ ዘመን ስለመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከልጅነታችን ጀምሮ አበክራ ታስተምረናለች፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤቶቿም ኮትኩታ አሳድጋ መንፈሳዊ ፍሬ ለማፍራት ታበቃናለች፡፡ ለዚህ የመሸጋገሪያ ዕድሜ በደረስንበት ጊዜም የሕይወታችን መርሕ የሆነው ትምህርተ ወንጌል እንዳይጓደልብን በዐውደ ምሕረቷ ላይ ጉባኤ ዘርግታ ሰማያዊ ኅብስትን አዘጋጅታ ትመግበናለች፡፡

በጉባኤያት የሚሰበኩ ትምህርቶች ለክርስቲያናዊ ሕይወት እንድንበቃ የሚረዱንና ለዘለዓለማዊ ሕይወት የሚያበቁን ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የምትመግበን ምግበ ሕይወት ግን በዚህ ብቻ አይወሰንም፡፡ ዘወትር መንፈሳዊ ዝለት አጋጥሞን ከቤቷ እንዳንርቅና በዓለም እንዳንጠፋ ዓለም ባፈራቻቸው የመገናኛ ብዙኀን በየቤታችን፣ በትምህርት ቤታችንና በየአካባቢያችን የሕይወትን ምግብ እየመገበች ታኖረናለች፡፡ ቅዱስ ቃሉን ሰምትንም ለሥጋ ወደሙ እንድንበቃ ምሥጢራቷን ታካፍለናለች፡፡

ለዚህም ተልእኮ ተደራሽነት በሀገራችን የመንፈሳዊ አገልግሎት ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ስፍራ የሚሰጠው ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤ አገልግሎቱ ውስጥ ለኦርቶዶክሳዊያን ወጣት ተማሪዎች ከሚሰጠው ሥርዓተ ትምህርት በተጨማሪ ከምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ይካፈሉ ዘንድ ዘወትር እሑድ የሚቀርበው “የሕይወት ቀን” ተጠቃሽ ነው፡፡ በዓመት በሁለቱ የአጽዋማት ወቅት በነቢያትና በዐቢይ ጾም የሚካሄደው ይህ አገልግሎት በአብዛኛው የከፍተኛ ተቋማት ተማሪዎች የሚሳተፉበት ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከማስተማር ባሻገር በንጽሕና ሕይወት ኖረው ለቅዱስ ቁርባን እንዲበቁ ለማድረግ ባለው ቁርጠኛ ሐሳብ  በጀመረው በዚህ መርሐ ግብር በተለይም በአዳማ፣ በሐሮማያ፣ በጎንደር እና በሌሎች ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚገኙ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን የንስሓ አባት ከማስያዝ ጀምሮ ሥጋ ወደሙ እንዲቀበሉ ይረዳቸዋል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሥጋዬን የበላ ደሜን የጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው” በማለት እንደተናገረው እኛ ክርስቲያኖች በንስሓ ሕይወት ተመላልሰን ለሥጋ ወደሙ እንድንበቃ የአምላካችን ቅዱስ ቃል ይገልጻልና የተማርነው ትምህርትም ይሁን የምንኖረው ክርስቲያናዊ ሕይወት ፍጻሜው ቅዱስ ቁርባን በመሆኑ ተማሪዎቹ ይህንን ተረድተው እንዲተገብሩት ማኅበራቸው ማኅበረ ቅዱሳን እገዛ ያደርግላቸዋል፡፡ (ዮሐ. ፮፥፶፫)

ይህን ተልእኮ ለመፈጸም በግቢ ጉባኤያት ለአገልግሎት የተመደቡ መምህራንና ሰባኬ ወንጌላውያን ተማሪዎቹን ለቅዱስ ቁርባን ዝግጁ እንዲሆኑ የእግዚአብሔርን ቃል ከማስተማር ባሻገር አስቀድመው በንስሓ አባቶቻቸው አማካይነት ንስሓን እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ ከዚህም ቀጥሎ ለአንድ ሳምንት ያህል ሥርዓተ ንስሓን የሚፈጽሙበት “የንስሓ ሳምንት መርሐ ግብር” ይከናወናል፡፡ ተማሪዎች አስፈላጊውን ሥርዓት ተከትለውና በምክረ ካህን ታግዘውም ቅድመ ዝግጅታቸውን ሲያጠናቀቁ ሥራ አስፋጻሚ ቢሮው ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ ጋር በመነጋገር በተለይም በዐበይት የአጽዋማት ወቅቶች ማለትም በዐቢይ ጾመና በጾመ ነቢያት ሥጋ ወደሙ ከሚቀበሉበት ዕለተ እሑድ ዋዜማ የአዳር መርሐ ግብር በማዘጋጀት ትምህርተ ወንጌልና ውይይት ያደርጋል፡፡

በመቀጠልም በቤተ ክርስቲያናቱ ተገኝተው ሥርዓተ ቁርባን እንዲካፈሉ ካደረገ በኋላ ከመምህራኑ ጋር በመተባበር ማኅበሩ የአጋፔ መርሐ ግብር አዘጋጅቶ ያቀርብላቸዋል፡፡ የአጋፔ መርሐ ግብሩንም ተከትሎ የተለያዩ መርሐ ግብራትን በማዘጋጀት የሕይወት ምግብን እንዲመገቡ ያደርጋል፡፡ ቀሪው ዘመናቸውን በሃይማኖት ጸንተው አንዲኖሩና እስከ ሕይወታቸው ፍጻሜ ድረስ ለቅዱስ ቁርባን የበቁ እንዲሆኑ ለመርዳት የድኅረ ጉባኤያት መርሐ ግብር አዘጋጅቶም የማያቋርጥ እገዛ ያደርግላቸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ያስመረቃቸው በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች የቀና መንፈሳዊ ሕይወትም ጉዳዬ ብሎ የያዘው ተልእኮው በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን በየጊዜው ይህን ሥራውን ለማከናወን የሚረዱ መርሐ ግብራትን ያዘጋጃል፡፡ በተለይም ተልእኮውን ተደራሽ ለማድረግ የሚረዱ የዐቅም ማጎልበቻ ሥራዎችና ለአገልግሎቱ ስኬት እክል የሚሆኑ ችግሮችን የመፍታት ሥራ እየሠራ ይገኛል፡፡ ማኀበሩ ለዚህ እንደ መነሻ ያደረገው በ፳፻፲፫ የተጠናው ጥናት እንደሚያሳየው ከሆነ የመምህራን አቅም ማጎልበቻ ሥልጠናዎች እጥረት፣ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የመማርያ ግብአቶች አለመሟላት እንዲሁም ሌሎች ውስጣዊ እና ውጫዊ ተግዳሮቶች በመሆናቸው ይህን ችግር ለመቅረፍ የሚያግዙትን ተግባራት በመለየት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡

ስለሆነም ይህን ተግዳሮት ለማከናወን ማኅበሩ የበጎ አድራጊ ግለሰቦችም ሆነ ድርጅቶች እገዛ እንደሚያስፈልጉት በማመን በዚህ በያዝነው የግንቦት ወር ባወጣው ዕቅድ መሠረት የ፳፻፲፭ ዓ.ም የግንቦት ልደታ ለማርያምንበዓል “ግንቦት ልደታን ለግቢ ጉባኤ” በሚል ርእስ መርሐ ግብር አዘጋጅቷል፡፡ በዋናው ማእከል ደረጃ ከሚያዝያ ፳፰/ ፳፻፲፭ ዓ.ም እስከ ግንቦት ፮ /፳፻፲፭ ዓ.ም ድረስ ይህ መርሐ ግብር ይከናወናል፡፡ በዋነኛነትም የማኅበሩን የ፴፩ ዓመት አገልግሎት የግቢ ጉባኤ ፍሬዎችን አስተዋጽዖ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለምእመናን፣ ለተማሪ ወላጆች፣ ለሀገር እና ለዓለም በማስተዋወቅ ነው፡፡

የማኅበረ ቅዱሳንን የግቢ ጉባኤያት መርሐ ግብርን መደገፍ የተማሪዎችን መንፈሳዊ ሕይወት መርዳት ብቻ ሳይሆን ጠቀሜታው ለሀገር፣ ለቤተ ክርስቲያንና ለሁላችንም ጭምር በመሆኑ ተገቢውን እገዛ የማድረግ ኃላፊነት አለብን፡፡ ለዚህም የአምላካችን የልዑል እግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ እንዲሆንልን በጸሎት ማሳሰብም ተገቢ ነው፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!

“በማርያም ልደት ዛሬ ደስታ ሆነ” (ቅዱስ ያሬድ)

በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግንቦት አንድ ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት የሚከበርበት ዕለት ነው፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልደት እግዚአብሔር አስቀድሞ በትንቢት፣ በምሳሌና በራዕይ የሰውን ልጅ ድኅነት በጉጉት ሲጠባበቁ ለነበሩ ነቢያት ገልጿል፡፡ በልዩ ልዩ ምሳሌዎችም መስለው ከፊታቸው ያለውን ዘመን አሻግረው በመመልከት ተናግረዋል፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ “ከዕሴይ ሥር በትር ትወጣለች፤ አበባም ከእርሷ ይወጣል፡፡” ብሎ ትንቢት የተናገረላት፤ ልበ አምላክ ዳዊት “የወርቅ ልብስ ተጎናጽፋ ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” ፤ ቅዱስ ዮሐንስም በራእዩ “ፀሐይን የተጎናጸፈች፣ ጨረቃን የተጫማች፣ አሥራ ሁለት ከዋክብት አክሊል በራሷ ላይ ያላት” በማለት ተባብረው የመሰከሩላት ቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደችባት ቀን ናት፡፡ (ኢሳ. ፲፩፥፩ ፤ መዝ. ፵፬፥፱፤ ራዕ. ፲፪፥፩)

ነቢየ እግዚአብሔር ሰሎሞን በመኃልየ መኃልየ ድርሰቱም “ንዒ እምሊባኖስ መርዓት ንዒ እምሊባኖስ፤ ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስ ከእኔ ጋር ነይ” እያለ ተናግሮላታል፡፡ ይህም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልደት በሊባኖስ ሀገር ስለመሆኑ ያመለክታል፡፡ (መኃ. ፬፥፰) በቅድስት ቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት መሠረት የእመቤታችን የትውልድ ስፍራ ሊባኖስ የተባለው ተራራማ ሀገር ነው፡፡

የእመቤታችንን የዘር ሐረግ ወደ ኋላ ሰባት ትውልድ ስንቆጥር ቴክታና ጴጥርቃ የተባሉ ባልና ሚስት ነጭ እንቦሳ ከበረታቸው ስትወጣ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ስትደርስ፤ ስድስተኛዪቱ ጨረቃን ጨረቃዋም ፀሐይን ስትወልድ በሕልም በማየታቸው በሀገራቸው ለሚገኝ መፈክረ ሕልም (ሕልም ፈች ሊቅ) ሄደው ነገሩት፡፡ “ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ፤ ጨረቃይቱ ከፍጡራን በላይ የምትሆን ልጅ ትወልዳላችሁ፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም” አላቸው፡፡ እነርሱም ጊዜ ይተርጉመው ብለውት ሄዱ፡፡ ከዚህ በኋላ ልጅ ወለዱ፡፡ ስሟንም “የተሳልኩትን አገኘሁ፤ የተመኘሁትን አገኘሁ” ሲሉ “ሄኤሜን” አሏት፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና ለአካለ መጠን ስትደርስ ከቤተ ይሁዳ ለተወለደ ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡

ኢያቄምና ሐና መካን ስለነበሩ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ጸልየው፤ ሲሰጣቸውም መልሰው ለእርሱ እንደሚሰጡ ስዕለትን ተስለው ነበር፡፡ ጸሎታቸው ሲደርስ ለሐና በሕልም የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጸላት፡፡ ፀዓዳ ርግብ ሰባቱ ሰማያትን ሰንጥቃ መጥታ በራሷ ላይ ተቀምጣ በጆሮዋም ገብታ በማሕፀኗ ስትተኛ አየች፡፡ ኢያቄምም በተመሳሳይ ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ዖፍ ወርዶ በራሱ ላይ ሲቀመጥ አየ፡፡ ሁለቱም በሕልም ያዩትን በመግለጥ ተነጋገሩ፡፡

ሐናም ፀነሰች፤ ሐና መጽነሷ በታወቀ ጊዜም የአርሳባንን ልጅ ዓይን በማብራቷና ሳሚናስ የሚባለውን የጦሊቅን ልጅ ከሞት በማስነሣቷ አይሁድ በቅናት ተነሳስተውባቸው ሊገድሏቸው እንደሚሹ ለሐናና ኢያቄም መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተገልጾ ስለነገራቸው ወደ ሊባኖስ ተራራ እንደሄዱ እና በጨረቃ የተመሰለች ድንግል ማርያም በሊባኖስ ተራራ እንደ ተወለደች የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡

ርግብ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትሆን፤ ፀዓዳ (ነጭ) መሆኗ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ዘላለማዊ ድንግልናዋ ነው፡፡ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማሕፀኔ ስትተኛ አየሁ ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን የምትፀንሰውን ንጽሕት ርግብ የተባለችውን እመቤታችንን የምትወልድ መሆኗን ሲያጠይቅ ነው፡፡

በሐዲስ ኪዳን ሊቃውንትም ትንቢተ ነቢያትንና ወንጌልን በማጣጣም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ልደት አመስጥረው አስተምረዋል፡፡ እንደ ምሳሌ ጥቂቶቹን ብንመለከት፡-  ቅዱስ ያሬድ “ማርያምስ ከጥንት ጀምሮ በአዳም ባሕርይ ውስጥ እንደ ነጭ ዕንቁ ታበራለች” ሲል ተናግሯል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በደፈረሰው ዓለም በንጽሕና፣ በቅድስናና በድንግልና ስታበራ መኖሯንና ኋላም የዓለም ብርሃን የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን መውለዷን አመስጥሮ ተናግሯል፡፡

አባ ሕርያቆስም በቅዳሴው “ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤ በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐናና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ” በማለት የድንግል ማርያምን በንጽሕና፣ በቅድስና መወለድ ተናግሯል፡፡

ሐና እና ኢያቄም ከአይሁድ ለማምለጥ ተሰደው በአድባረ ሊባኖስ ሥር እመቤታችንን ወለዱ፡፡ በወቅቱ ከቤት የወጡት ለሽሽት ነበርና ስንቅ ስላልያዙ ምግባቸው ንፍሮና ጥራጥሬ ነበር፡፡ ይህንን ትውፊት በመያዝ ምእመናን ንፍሮ አዘጋጅተው በዝማሬና በእልልታ እንደሚያከብሩት ሁሉ አንዳንዶች ባልተገባና ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ባፈነገጠ ሁኔታ ሲያከብሩትም እየተለመደ መጥቷል፡፡ ይህ አካሄድ ፍጹም ተገቢ ባለመሆኑ ሊታረም የሚገባው ነው፡፡

በእውነት የእርሷ ልደት የልዑል እግዚአብሔር ማደሪያው መቅደስ የተሠራባት፣ የነቢያት ትንቢት የተፈፀመባት፣ የብሉይ ኪዳን ማብቂያ የሐዲስ ኪዳን መጀመሪያ ናትና ልደቷ ለሰው ልጆች ሁሉ (ለሕያዋን ሁሉ) ታላቅ የደስታ ቀን በመሆኑ ሁላችንም “ዮም ፍስሐ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም፤ እነሆ ዛሬ በእመቤታችን ልደት ደስታ ሆነ” እያልን በዝማሬ እናመስግናት።

የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን እና ግቢ ጉባኤያት

ክፍል ሁለት

ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ በይፋ ዕውቅና ተሰጥቶት በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ሆኖ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ መሠረት አድርጎ የአገልግሎቱን ትኩረት  በዋናነት ግቢ ጉባኤያት ላይ አደረገ፡፡ በዚህም መሠረት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎችን ከመደበኛው ትምህርታቸው ውጪ በየአጥቢያቸው የሚገኙ  የስብከተ ወንጌል አዳራሾችን በመጠቀም፣ አዳራሽ የሌላቸም በዛፍ ሥር እየተሰባሰቡ መምህራንን በመመደብ መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከሰ/ት/ቤቶች ጋር በመቀናጀት ማስተማሩን ቀጠለ፡፡

ከ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ጀምሮም ሥርዓተ ትምህርት በመቅረጽ ፳፪ የትምህርት ዓይነቶችን በመለየት ለእያንዳንዱ የትምህርት ዓይነትም መጻሕፍትን በማዘጋጀት ተማሪዎች ቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸውን፣ አስተምህሮዋን እና አገልግሎቷን እንዲረዱ፣ ከተለያዩ ያልተገቡ ጠባያት ምግባራት ርቀው እውነተኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንዲሆኑና በመደበኛ ትምህርታቸውም ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ ከፍተኛ ጥረት ተደረገ፡፡

በየጊዜውም የሚሰጡ የትምህርት ዓይነቶችን፣ የተማሪዎችን አቀባበል እና አፈጻጸማቸውን በመገምገም በድጋሚ አዲስ ሥርዓተ ትምህርት እንዲዘጋጅ በማስፈለጉ በ፳፻፬ ዓ.ም የትምህርት ዓይነቶቹን በመከለስ ወደ ፲፩ ዝቅ እንዲሉ ተደርገዋል፡፡ መምህራንን በየማእከላቱ በመደበኛነት እና በበጎ ፈቃደኝነት እንዲያስተምሩ፤ ከዚያም አልፎ ከተማሪዎች ውስጥ የተተኪ መምህራን እና የአመራር ሥልጠና ወስደው በየግቢያቸው በመመደብ፣ አፈጻጸሙንም በመከታተል ውጤታማ ሥራ ተሠርቷል፡፡ በዚህም ተማሪዎች ተመርቀው ሲወጡ በሥነ ምግባር የታነጸ ትውልድ በመፍጠር የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አደራ ተቀብለው እንዲወጡ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችና በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የአንገት ማተብና መስቀል ይደረግላቸዋል፡፡

ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በከፍተኛ ውጤት የሚመረቁ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችም “ለውጤታማነታችን ትልቁን ድርሻ የሚወስደው ማኅበረ ቅዱሳን ነው” በማለት የተሸለሙትን  ሜዳልያ እና ዋንጫቸውን ለማኅበረ ቅዱሳን በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜም የተሸለሙትን ሜዳልያ ለማኅበረ ቅዱሳን በመስጠት በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የኩላሊት ንቅለ ተከላ ሒኪም የሆኑት ፕሮፌሰር እንግዳ አበበ ይጠቀሳሉ፡፡ ወደ ሥራ ሲሠማሩም ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋ መልሰው ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ፣ በሚሠማሩበት የሥራ መስክም በታማኝነትና በቅንነት እንዲያገለግሉ አስችሏቸዋል፡፡ በቅድስት ቤተ ክርሰቲያን መዋቅር ውስጥ በመግባትም በሰ/ት/ቤቶች እና በሰበካ ጉባኤያት እንዲሁም በአብነት ትምህርት ገፍተው ዲቁና ተቀብለው የሚወጡትም በቤተ ክርስቲያን በውስጥ አገልግሎት እንዲሳተፉ ማድረግ ተችሏል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከተከታታይ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት በተጨማሪ በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ አማካይነት “ጉባኤ ቃና” የተሰኘ ተማሪ ተኮር መረጃዎችን የያዘ መጽሔት ከ፳፻ ዓ.ም ጀምሮ በማሳተምና መልሶ ለተማሪዎች በማሠራጨት፣ በምረቃ መጽሔት፣ በድረ ገጽ፣ በፌስቡክ፣ በቴሌግራም ሃይማኖታቸውን ጠንቅቀው እንዲረዱ እገዛ ሲደረግላቸው ቆይቷል፡፡

በበጎ አድራጎት ተግባራትም የመንፈሳዊ ጉዞ መርሐ ግብር፣ ነዳያንን መመገብ፣ አረጋውያንን መንከባከብ፣ ለሕፃናት የማጠናከሪያ ትምህርት በመስጠት፣ አብያተ ክርስቲያናት እና የስብከተ ወንጌል አዳራሾችን በማነጽ፣ … ወዘተ ተግባራትን በማከናወን ረገድ ግቢ ጉባኤያት አርአያ የሚሆኑ ሥራዎችን ሠርተዋል ወደፊትም በተጠናከረ ሁኔታ ይቀጥላሉ፡፡

ግቢ ጉባኤያትን ለማስተማርና ብቁ ዜጋ አድርጎ ለመቅረጽ የማኅበረ ቅዱሳን ድርሻ ከፍተኛውን ቦታ የሚይዝ ሲሆን እንዚህን ሥራዎች ለመሥራት በሚደረገው ጥረት ውስጥ በርካታ ችግሮችም በእግዚአብሔር ቸርነት ታልፈው ዛሬ ላይ መድረስ ተችሏል፡፡ ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህልም፡-

ውጫዊ ችግሮች ከምንላቸው ውስጥ፡- ዓለማዊነትና ሉላዊነት/Globalization/ አስተሳሰብ መስፋፋት፣ የመገናኛ ብዙኀንና ማኅበራዊ ሚዲያዎች መስፋፋት፣ የምዕራባዊ የባሕል ወረራ፣ የተማሪዎች ከኢትዮጵያዊነት እሴት ማፈንገጥ/ ውርጃ፣ ሱሰኝነት፣ ግብረ ሰዶም፣ ዝሙት፣ ሌሎችም መስፋፋት/፣ የአጽራረ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ እና የጎሣ ፖለቲካ አስተሳሰብ መስፋፋት ይጠቀሳሉ፡፡ ውስጣዊ ችግሮችን ስንመለከት ደግሞ፡- የግብረ ገብነት መቀነስ፣ የሙስና መስፋፋት፣ ለሱስ ተጋላጭ የሆኑ ወጣቶች መበራከት፣ ዓለም አቀፋዊና ማኅበራዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ የቤተ ክርስቲያን ተሳትፎ አናሳ መሆን፣ ለግቢ ጉባኤያት አገልግሎት በብዛትና በጥራት በተለያዩ ቋንቋዎች የሚያገለግሉ አገልጋዮች እና መምህራን ያለመኖር እንደ ችግር የሚታዩ ናቸው፡፡

ግቢ ጉባኤያት ማኅበረ ቅዱሳን ወደፊት አገልግሎቱን በማጠናከር ተቋማዊ ለውጥን በመተግበር የሚታዩ ችግሮችን በመፍታት ልዩ ትኩረት ሠጥቷቸው ከሚሠራባቸው ዘርፎች አንዱ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የጉባኤ ቤት ደቀ መዛሙርትን ለግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማሠልጠን፣ ኢ-መደበኛ መምህራንን በማእከላት ማፍራት፣ መደበኛ መምህራንን እና የአብነት መምህራንን መቅጠር፣ ከአንድ በላይ ተጨማሪ ቋንቋ ለሚያስተምሩ እና ለሚያሠለጥኑ መምህራን የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና መስጠትና ማሠማራት፣ ተተኪ መምህራንን በደረጃ ፫ በልዩ ሁኔታ ማሠልጠን፣ ግቢ ጉባኤያት ተኮር የአንድ ሰዓት የብሮድ ካስት መርሐ ግብር ሥርጭት መጀመር እና የመሳሰሉት አገልግሎቶች ተግባራዊ ይደረጋሉ፡ ፡ በዚህም የወደፊት ተስፋችን በቅንነትና በታማኝነት ሀገርንና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚረከቡ እንዲሁም ሊያገለግሉ የሚችሉ በሁለት ወገን ማለትም በዓለማዊውም ሆነ በመንፈሳዊው ዘርፍ የተሣለ ሰይፍ ሆነው የሚወጡ ወጣቶችን ማፍራት ነው፡፡

በዚህም መሠረት የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎት ለማጠናከር “ግንቦት ልደታን ለግቢ ጉባኤያት” በሚል መሪ ቃል ከሚያዚያ ፳፰ እስከ ግንቦት ፮ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ልዩ ልዩ መርሐ ግብራትን በማዘጋጀት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ በተለይም በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ውስጥ የሚያጋጥመው የፋናንስ እጥረት ለመቅረፍ ከበጎ አድራጊ ምእመናን፣ ከግቢ ጉባኤያት ተመርቀው በልዩ ልዩ ሥራ ላይ የሚገኙ ወንድሞችና እኅቶች፣ ሌሎችም ተባባሪ አካላት ድጋፍ ለማሰባበሰብ እየሠራ ይገኛል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር 

ግቢ ጉባኤያት በቤተ ክርስቲያን

ቅዱስ ያሬድ “ሀገረ ክርስቶስ አዳም ወሠናይት ከመ ፀሐይ ብርህት ወከመ መርዓት ሥርጉት፤ የክርስቶስ ሀገር በጣም ያማረች፣ እንደ ፀሐይ የበራች እንደ ሙሽራም የተሸለመች ናት” በማለት የሚገልጻት ቤተ ክርስቲያን እናት ልጇ ምግብ አልበላላት ሲል ከምትጨነቀው ጭንቀት የበለጠ እናት ቤተ ክርስቲያን ከደገሰችው ድግሥ ልጆቿ አልመገብ ሲሉ ዘወትር ታዝናለች ትተክዛለች።(ጾመ ድጓ ዘምኵራብ)

የደገሠችልን ድግሥም ዛሬ በልተነው ነገም የሚያሻን አብዝተን ብንበላው ሕመም የሚያመጣብን ሳይሆን ከማርና ከስኳር ይልቅ ለሕይወታችን አስፈላጊ የሆነውን የእግዚአብሔር ቃል፣ ሕይወት የሚሆነን ሥጋ ወ-ደሙን ነው።

ነገር ግን የመጀመሪያው ሰው አዳም “በገነት ካለው ዛፍ ሁሉ ብላ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያሳየውና ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትምታለህና፡፡” ተብሎ የተነገረውን ትእዛዘ እግዚአብሔር በመተላለፍ በልቶ የሞት ሞትን እንደሞተ ሁሉ ዛሬ ደግሞ ሥጋዬን ብሉ ደሜን ጠጡ በሕይወትም ትኖራላችሁ ቢለንም ባለመብላት ወደ ሞት መንገድ ጉዞ የጀመርን ብዙዎች ነን። ((ዘፍ. ፪፥፲፮-፲፯)

መድኃኒት የሚያሻው ለታመመ እንደሆነ ሁሉ በኃጢአት የታመመ ብዙ ነው፡፡ በተለይም ወጣቱ ትውልድ ግንባር ቀደሙን ቦታ ይይዛል። ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚገቡ ተማሪዎች ከተለያዩ አካባቢዎች እንደመሰባሰባቸው የተለያየ የሕይወት ተሞክሮ ያላቸው በመሆኑ ልጓም የሚሆናቸው መንፈሳዊ ዕውቀት ካላገኙ በተለያዩ የኃጢአት ደዌያት እንደሚያዙ የሚያጠራጥር አይደለም።

ከቤተሰብ፣ ከዘመድ ርቀው በመኖራቸው ነፃነት ስለሚያገኙ ከመንፈሳዊው ሕይወት ይልቅ መጥፎ በሆነ ሱስ ራሳቸውን የሚደብቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ በሥጋዊ ሥራዎች (በዝሙት፣ በምንፍቅና፣ በዘረኝነት) በሽታ ተይዘው ክርስቲያናዊ ሕይወታቸውን፣ ኢትዮጵያዊ ማንነታቸውን ያጣሉ። ይህን ፈተና እንዲቋቋሙ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን በተደራጀ መንገድ እንድትቀጥል ግቢ ጉባኤ ሰፊውን ድርሻ ይይዛል።

ግቢ ጉባኤያት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓቷና ትውፊቷን ይዛ ከማስቀጠል አንጻር ምን ሠራ?

ቤተ ክርስቲያን ማለት እያንዳንዱ ምእመን፣ ሕንጻው፣ ኅብረታችንን ማለታችን እንደሆነ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታየ “ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን” በሚለው መጽሐፋቸው ገልጸውታል። የመጀመሪያው እያንዳንዱ ክርስቲያን ትውልድ እንዲቀጥል የድርሻውን እንዲወጣ ማድረግ ነው። እያንዳንዱ ክርስቲያን እንዲቀጥል ማድረግ  ማለት  አባት  እናት  ሲሞት ልጅ  ይተካል። ተተኪው ትውልድ ከሚባለው ውስጥ ደግሞ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚያልፉት  ይገኙበታል። ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም አስተምህሮዋን ዶግማዋን ቀኖናዋን እና ትውፊቷን ይዛ የምትቀጥለው ርትዕት የሆነችውን  የአባት  የእናቱን  ሃይማኖት  ጠንቅቆ  ባወቀ  ትውልድ  ነው።  ለዚህ ደግሞ  ግቢ  ጉባኤያት  አስፈላጊ  ናቸው።

ሁለተኛው የክርስቲያኖች ኅብረት ነው። እያንዳንዱ ክርስቲያን ትውልዱን ማስቀጠል ከቻለ የክርስቲያኖች ኅብረትም ይቀጥላል፡፡ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሰባሰቡ ተማሪዎች ከሀገራችን ከሁሉም  አቅጣጫ የሚመጡ  ስለሆነ  ግቢ ጉባኤያት  ላይ  በሚገናኙበት  ወቅት የአኗኗር ባህላቸው ሳያግዳቸው እርስ  በእርሳቸው  ተግባብተው አንዱ ከሌላው እየተማረ በሃይማኖት፣ በምግባር በጎ  ነገር  የሚማሩበት ነው። ስለዚህ ሰው ከጎረቤቱ ጋር መኖር በከበደው በዚህ ዘመን ኢትዮጵያዊ አንድነት ብለን የምናቀነቅነውን ሐሳብ እየታደጉ ያሉት እነዚህ  የግቢጉባኤያት ተማሪዎች ናቸው።

በክርስቲያናዊ መዋደድ የሚዋደዱ፣ የሚረዳዱ፣ የሚተሳሰቡ ተማሪዎችን ብንፈልግ ከፍ ያለውን ቦታ የሚይዙት የግቢ ጉባኤያት ፍሬዎች ናቸው። ለማኅበራዊ አንድነትም ከፍ ያለ አስተዋጽኦ እንዳለው በዚህ መረዳት ይቻላል። የክርስቲያኖች ኅብረት እንዲታነጽ፣ እንዲቀጥል ያደርጋልና።

ሦስተኛው፡- ክርስቲያኖች እስካሉ ድረስ ሥርዓተ አምልኮን ለመፈጸም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መኖር አለበት። ቤተ ክርስቲያን የምትታነጸውም በሃይማኖቱ በጸና፤ አስተምህሮዋን ተረድቶ ለአገልግሎት ራሱን ባዘጋጀና ለሌሎች ፍቅር በሚሰጥ፣ ዛሬን ብቻ ሳይሆን ወደፊትን አሻግሮ ማየት በሚችል ትውልድ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ግቢ ጉባኤያት ከፍ ያለ አበርክቶት አላቸው።

ዛሬ ላይ በግቢ ጉባኤያት ያለፉ ልጆች አንዳንዶቹ አራቱ ባሕርያተ ሥጋ ተስማምተውላቸው ዓለምን ንቀው መንነው ለሀገር ሰላም እና አንድነት ይለምናሉ፤ አንዳንዶቹ በሥርዓተ  ቤተ ክርስቲያን ጸንተው  በዲቁና፣ በሕግ እየኖሩ ማለትም (በቅስና) እያገለገሉ ይገኛሉ። አንዳንዶች የዘመናዊ ትምህርታቸውን እንደጨረሱ ጉባኤ ቤት ገብተው የሚማሩም አሉ። የተማሩት ደግሞ እንደ አባቶቻቸው ወንበር ተክለው የሚያስተምህሩም አሉ።

በሃይማኖት ዐይን ለተመለከተው ይህ ቀላል የሚባል አይደለም። “ግንቦት ልደታን ለግቢ ጉባኤ” በማለት ሳምንቱ የግቢ ጉባኤ ሳምንት እንዲሆን የተደረገውም እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ ወደፊት ግቢ ጉባኤ ከዚህ የተሻለ አሠራር እንዲኖረው ለቤተ ክርስቲያን፣ ለሀገር የሚጠቅም ትውልድ ለመፍጠር በማሰብ ነው።

የአንድ ሳምንት የገንዘብ ማሰባሰብ ዓላማውም ቅዱስ ጳውሎስ “ስለዚህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉምና።”  (፪ኛጴጥ. ፩፥፲) እንዲል በአእምሮ የጎለመሱ፣ በጥበብ ያደጉ፣ ዘመኑን የዋጁ የቤተ ክርስቲያንን ልጆች የበለጠ ማትጋት ስለሚያስፈልግ ግቢ ጉባኤያትን ማጠናከር ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር በመሆኑ የግቢ ጉባኤ ባለአደራዎች የተጣለባችሁን ኃላፊነት እና አደራችሁን ተወጡ።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር