ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል ሁለት

በዲ/ መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

የጾም ዓይነቶች

የጾም ዓይነቶች ሁለት ናቸው እነርሱም የአዋጅ እና የፈቃድ በመባል ይታወቃሉ፡፡

. የዐዋጅ ጾም

የዐዋጅ ጾም የሚባሉት በዐዋጅ ለሁሉም ሰው ማለት ከሰባት ዓመት በላይ ለሆነ ሰው ሁሉ የሚታወጅ እና በይፋ ሁሉም ተባብሮ ስለሚጾማቸው ነው፡፡ “በጽዮን መለከትን ንፉ፥ ጾምንም ቀድሱ፥ ጉባኤውንም አውጁ፥” (ኢዩ ፪፥፲፭) እንደተባለ አንዴ በቤተ ክርስቲያን ታውጆ ሥርዓት ተሠርቶለት የሚጾም ስለ ሆነ የአዋጅ ጾም ይባላል፡፡ የአዋጅ ጾም በማለት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምታውጃቸው እና ሁላችን በጋራ የምንጾማቸው አጽዋማት ሰባት ሲሆኑ እንደሚከተለው እንመለከታቸዋለን፡-

  1. ዓቢይ ጾም (ጾመ ሁዳድ)
  2. ጾመ ድኅነት (ዓርብ እና ረቡዕ)
  3. ጾመ ሐዋርያት (የሰኔ ጾም)
  4. ጾመ ፍልሰታ
  5. ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)
  6. ጾመ ነነዌ
  7. ጾመ ጋድ ናቸው፡፡

. የፈቃድ ጾም

የፈቃድ ጾም የሚባለው ሁሉም ሰው በዐዋጅ ሳይታዘዝ በፈቃዳችን የምንጾማቸው ናቸው፡፡ በቀኖና የሚሰጠን ጾም የሚመደበው ከዚህ ውስጥ ነው፡፡ አንዳዴም በተለየ ሁኔታ ለራሳችን የምንጾመው ጾምም የፈቃድ ይባላል፡፡ ለምሳሌ ጾመ ዮዲት (ጳጉሜን ላይ የሚጾም) እና ጾመ ጽጌ የሚጾሙ አሉ፤ እኒህም የፈቃድ አጽዋማት ናቸው፡፡

ውድ ተማሪዎች ጾም ፍቅርን ለእግዚአብሔር መግለጫ በመሆኑ ከልባችን ወደነው መጾም ይገባል፡፡ በጾም ስሜትን ራስን እንገዛበታለን፡፡ ጾም መንፈሳዊ ኃይልን ታጎናጽፋለች፤ አጋንንትን ለማራቅ እጅግ ትጠቅመናለች እንዲሁም ለመንፈሳዊ አገልግሎት የበረታን ታደርገናለች እና በአግባቡ በመጾም የምታሰጠውን ዋጋ ለማግኘት እንትጋ፡፡

እንደ ግብዞች አትጠውልጉ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዴት መጾም እንዳለብን የተራራውን ትምህርት ባስተማረበት ወቅት እንዲህ በማለት ተናገሮ እንመለከታለን “ስትጦሙም፥ እንደግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮)። በዚህ ንባብ ግብዞች የሚለውን ቃል በሁለት መልኩ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስቀምጦት ይገኛል። እነዚህም፡-

 ፩. መጦመቸው እንዲታወቅላቸው ፊታቸውን የሚያጠፉ እንዲሁም ይጠወልጋሉ። እነዚህ ጦማቸውን ዋጋ ለሚከፍል እግዚአብሔር ከማሳየት ይልቅ ለሰዎች አድናቆት ለማግኘት ሲሉ ብቻ የጾምን ዓላማ ያጠፉታል።

፪. ሳይጾሙ እንደጾሙ የሚያስመስሉ ከንፈራቸውን የሚያደርቁ ግብዝ ተብለው ተጠርተዋል። የምንጾመው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትን ለማድረግ ነው እንጂ ውዳሴ ከንቱን ለማግኘት አይደለም፤ በሁለቱም መልክ የተገለጡት ግብዞች ግን የጾምን ዓላማ የረሱና ያልተገነዘቡ ናቸው። በግብዝነት የሚገኘው ደስታ ጊዜያዊና ወዲያው የሚረሳ ነው ሆኖም ቅጣቱ ከባድ መሆኑን ዐውቆ መጠንቀቅ ይገባል።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በተለይ በልቶ ማስመሰል ውዳሴ ከንቱን መፈለግ ብቻ ሳይሆን ውሸትንም በውስጡ የያዘ ነውና ከግብዝነት በመራቅ በእውነት ለጾም ሕግና ሥርዓት ልንገዛ ይገባል። ለቤተሰብ ለጓደኛ ለቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ራሳችንን በውሸት ሕጋዊ አድርገን ለማሳየት ስንል መንግሥተ እግዚአብሔርን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይገባል። ለሰው ጾመኛ ከመምሰል በመታቀብ ዋጋ ለሚከፍለው ጌታ ራስን ማሳየት ያስፈልጋል። ፊትን በማጥቆር ከመጾም ፊትን ከእግዚአብሔር የሚያገኙትን ዋጋ በእምነት በተስፋ በመጠበቅ ብሩህ ማድረግ በእጅጉ ይገባል። ጌታችን ጾሞ እንዴት መጾም እንዳለብን አስገንዝቦናል በዚያው መሠረት በመጾም ሥርዓትን ልንፈጽም ይገባል።

ክርስቶስ አምላካችን ዐርባ ቀንና ሌሊት በመጾም ጾም የመልካም ሥራ መጀመሪያ እንድትሆን ሰጥቶናል። እኛም የሐዋርያቱን ትውፊትና ኑሮ መሠረት በማድረግ ያማረ የጾም ሕግን ከትውልድ ትውልድ እንቀባበለዋለን። ጌታችን የጾመው በቁዔት አገኝበታለሁ ብሎ ሳይሆን አጋንንትን፣ የኃጢአት ሥሮች የተባሉ ትዕቢት፣ ስስት እና ፍቅረ ነዋይን የምናሸንፍበትን ሕግ ሊሠራልን እና ተግባሩን ሊያመለክተን ነው እንጂ ጾማችሁን ሁሉ ጾሜላችኋለሁ ከዚህ በኋላ መጾም አይጠበቅባችሁም ለማለት አይደለም።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በግቢ ሕይወታችሁ ከብዙ ማኅበረሰብ ጋር እንደመኖራችሁ በሃይማኖት ከማይመስሉን በተለይ ከመናፍቃን ጥያቄ ሊቀርብልን ይችላል። ለምሳሌ አጽዋማት ለድኅነት አያስፈልጉም አንዴ ክርስቶስ ጾሞልናል፤ በዚህ ጊዜ እንድትጾሙ የተጻፈው የት ነው? ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም የሚለውን ሕግ ጥሳችኋል ሊሉን ይችላሉ።

ውድ ተማሪዎች ከመናፍቃን ጋር ያለን ልዩነት ሰፊና የመዳናችን መንገድ ላይ መሆኑን ልብ ማለት አለባችሁ ይህ ማለት ከላይ የጠቀስነው ንግግራቸው የሚመነጨው እምነት ብቻ ከሚለው አስተምሮአቸው ነው። ምግባር ለድኅነት አያስፈልግም በጸጋው ብቻ ድነናል ከሚለው አቋማቸው መሆኑን በመረዳት ከእነርሱ መራቅ ሐሳባቸውን አለመስማት ይኖርብናል። ምክንያቱም ጾም ትእዛዘ እግዚአብሔር ናት፤ ምግባር የእምነት ነፍስ ናትና “መጽሐፍም፦ አብርሃምም እግዚአብሔርን አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቈጠረለት ያለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ። ሰው በእምነት ብቻ ሳይሆን በሥራ እንዲጸድቅ ታያላችሁ። … ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደ ሆነ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው።” (ያዕ. ፪፥፳፫-፳፮) እንደተባለ። እምነት ከምግባር ተዋሕዶ ሊገኝ ግድ ነው። እንግዲህ ከምግባራት ቀዳሚዋ ጾም መሆንዋ ደግሞ ሊዘነጋ አይገባውም። ጌታችን ስለ ሆድ ማሰብ ሞት እንደሆነ አስተምሮናል አስቀድመን ማሰብ የሚገባን ስለ ጽድቅ መሆኑንም አሳስቦናል “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፥ ይጠግባሉና።” (ማቴ. ፭፥፮)። “ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?” (ማቴ. ፮፥፳፭)።

ስለዚህ ክርስቶስ ጾሞልሃል የሚለውን የሰይጣን ትምህርት ትተን “ከመዝ ግበሩ፤ እንዲህ አድቡ” የሚለውን የክርስቶስን ድምጽ በመስማት የተወልንን የአርአያነት መንገድ በመከተል እውነተኛ በጎቹ ልንሆን ይገባል። “ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል።” (ማቴ. ፮፥፴፫) “ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮።)  ‘ይህም ሁሉ’ የተባለው ምግብን እና መሰሎቹን ነው። ክርስቶስ አትጹሙ አላለም ስትጾሙ እንደ ግብዞች አትሁኑ በማለት አጿጿሙን ተናገረ እንጂ ስለዚህ ጾም ክርስቶሳዊ ትእዛዝ ነው።

ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም በማለት ሆድን አምላክ በማድረግ ሊሾሙብን እንደ ሔዋን ራቁታችን ሆነን ገነትን መንግሥተ ሰማይን አጥተን እንዳንጠፋ መጠንቀቅ አለብን።  ውድ ተማሪዎች ተመልከቱ ጌታችን ስለ እጅ ንጽሕና ሲጨነቁ ስለ አመጋገብ ወጋቸው ከሕገ መጽሐፍ በላይ ሲያሳስባቸው ተመልክቶ የተናገራቸውን ነገር “እርሱም፦ እናንተ ደግሞ እንደዚህ የማታስተውሉ ናችሁን? ከውጭ ወደ ሰው የሚገባ ሊያረክሰው ምንም እንዳይችል አትመለከቱምን? ወደ ሆድ ገብቶ ወደ እዳሪ ይወጣል እንጂ ወደ ልብ አይገባምና አላቸው። እርሱም አለ፦ ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው። ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ ሐሳብ፥ ዝሙት፥ መስረቅ፥ መግደል፥ ምንዝርነት፥ መጐምጀት፥ ክፋት፥ ተንኰል፥ መዳራት፥ ምቀኝነት፥ ስድብ፥ ትዕቢት፥ ስንፍና ናቸውና፤ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል ሰውን ያረክሰዋል።” (ማር. ፯፥፲፰-፳፫)። ተማሪዎች ተመለከታችሁን? ይህ ጾምን የሚያጸና እንጂ የሚሽር ነውን? አይደለም ምክንያቱም ጾም ማለት ከምግብና ከሚያረክሶ ነገሮች ሁሉ መራቅ ነው።

በአጠቃላይ ከመናፍቃን ራሳችንን እንጠብቅ በተዋበች የጾም ሕግ ጽድቅን እንፈልግ፤ ከተድላ ደስታ በመራቅ ከእግዚአብሔር ጋር አንድ እንሁን “ትእዛዙንም የሚጠብቅ በእርሱ ይኖራል እርሱም ይኖርበታል፤ በዚህም በእኛ እንዲኖር ከሰጠን ከመንፈሱ እናውቃለን።” (፩ኛዮሐ. ፫፥፳፬ እንደተባለ። በተጨማሪም ምሳሌውን አርአያነቱን በማስተዋል እንከተል “በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል።” (፩ኛዮሐ. ፪፥፮) ተብሎ እንደተጠቀሰ።

የአጽዋማትን ጊዜ የተመለከተውን ልንወዛገብበት አይገባም። ውድ ተማሪዎች የእኛ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሥርዓተ አምልኮ ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ አይደለም ይልቁንም የቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት፣ ትውፊትና ከሐዋርያት ጀምሮ ያሉ አበው ትምህርት ሕይወት እንደ ምንጭ የሚወሰድ በመሆኑ ከበቂ በላይ ማስረጃ አለን። በሐዲስ ኪዳን ቀኖና ውስጥ ያሉ ስምንቱ መጻሕፍት ሁሉም ላይ የጾም ጊዜ ሥርዓት በቀኖናው ተጽፎ እንደሚገኝ መዘንጋት አይገባም።  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Top of Form

Bottom of Form

Top of Form

Bottom of Form

ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል አንድ

በዲ/ መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

ጾም ለሰውነት የሚያምረውን እና የሚያስጎመዠውን ነገር ሁሉ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ብሎ  መተው፣ ራስን በመግዛት ጣዕመ ዓለምን በመናቅ እግዚአብሔርን መከተል ማለት ነው፡፡ ጾም  ራስን ከክፉ ሥራዎች ሁሉ በማሸሽ የመንፈሳዊ ተጋድሎ መፈጸሚያ መሣሪያ እና የሥጋ ልጓም ነው፡፡ መንፈሳዊ በረከትን ለማግኘት ለትእዛዘ እግዚአብሔር ራስን ማስገዛት ነው፡፡ ፍጹም የሆነ የእግዚአብሔርን ርዳታ ማግኛ የፍቅር መንገድ ነው፡፡ ጾም ሃይማኖትን መግለጫ በተግባር ማሳያ መታመኛ መሣሪያ ነው፡፡ ጾም፤ ወዶ ፈቅዶ ምግብን በጊዜ ገደብ ጥሉላትን በቀናት/በወራት ገደብ እንዲሁም ነፍስን ከሚያሳድፉ ክፉ ሥራዎች መከልከል ነው፡፡ ለእግዚአብሔር ያለን ፍጹም ፍቅር የሚገለጠው በጾም በጸሎት እና ምጽዋት ነው፡፡ የቀና እና የተስተካከለ መንፈሳዊ ሕይወትን ከሚያደናቅፉ ማናቸውም እኩይ ተግባራት መራቅ እና መከልከል ጾም ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ነፍስን ሊያቆስላት የሚችለው ምንድን ነው? ስንል መልሱ የሥጋ ፈቃድን መፈጸም፣ በደል፣ ኃጢአትነው የሚል ይሆናል፡፡ ሰው ተማሪ ቢሆን ሠራተኛም ቢሆን በምንም ዓይነት ሥራ እና ሁኔታ ላይ ቢሆን ክርስቲያናዊ ሕይወቱን ለማረም ዕለት ዕለት መንፈሳዊ ተግባራትን መተግበር ያስፈልጋል፡፡ በይበልጥ ሐዋርያት የሥራ መጀመሪያ ያደረጓትን ጾምን እኛም አጥብቀን ልንይዝ ይገባል፡፡ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፥ ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው።” (ሮሜ. ፰፥፮)፡፡ ሥራችንን ክርስቲያናዊ ጉዞአችንን ፍጹም የሚያደርግልን ጾም ነው፡፡ ለዚህም ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን እንደ ምሳሌ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ስለዚህ ተማሪዎች ቀዳሚት ትእዛዝ የሆነች ሕግን ገንዘብ በማድረግ ሕይወታችንን ሰማያዊ ዋጋ በሚያሰጥ መልክ እንምራ፡፡

ጾምን ለምን እንጾማለን?

ጾም በመጀመሪያ ለሰው የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ የሰው ልጅ ቢመራበት የዘላለምን ሕይወት የሚወርስበት ልዩ የእግዚአብሔር የፍቅር ሕግ ነው፡፡ ሰው ፍትወቱን በዚህች ባማረች ሕግ ገዝቶ ዓይኑን ክፉ ከማየት፣ ጆሮውን ክፉ ከመስማት፣ ምላሱን ክፉ ከመናገር ከማማት፣ እግሩን እጁን ከመስረቅ ደም ለማፍሰስ ወደ ክፉ ከመገስገስ ቢከለክል ዋጋው ምንኛ ያማር ይሆን ነበር፡፡ እኛ በዚህ ዘመን ያለን ወጣቶች በዓለሙ ካለ ክፋት የትኛውን ተጸይፈን እንተዋለን? ዘመነኛው ቴክኖሎጂ ያመጣልንን ማኅበራዊ ሚዲያ በመጠቀም ክፉኛ ወደሚያቆስለን ለገሃነም ወደሚሰጠን የሥጋ ሥራ አዘንብለናል፡፡ ነገር ግን የተሰጠንን በጎ አእምሮ በመጠቀም ወደ ኃጢአት ከመሄድ ራሳችንን ልንጠብቅ እና ልናነጻ ይገባል፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ የጾምን ጥቅም በቅደም ተከተል እንመልከት፡–  

. ኃይለ እግዚአብሔርን ለማግኘት

አብዝቶ መመገብ ፈቃደ ሥጋ በፈቃደ ነፍሳችን ላይ እንዲሰለጥን ሰፊ በር ይከፍታል፡፡ ፍትወታተ ሥጋ እንዲሰለጥኑብንም ዋነኛ ሞተራቸው በመሆን ይጠቀሳል፡፡ ጥጋብን፣ ትዕቢትን፣ ንዝህላልነትን፣ ዝሙትን በማምጣት መንፈሳዊ ፍሬን እንዳናፈራ ያግደናል፡፡ ሰዶምን በእሳት እንድትቃጠል ካደረጓት ምክንያቶች አንዱ እንጀራን መጥገብ እንደሆነ (ሕዝ. ፲፮፥፵፱) ተገልጧል፡፡ ፈቃደ ሥጋችን በፈቃደ ነፍሳችን ላይ ኃይል እንዳይኖረው ጾም መጾም እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነቢዩ ዳንኤል ከሦስቱ ሕፃናት ጋር ከኢየሩሳሌም ተማርከው ወደ ናቡከደነፆር ግዛት ከተወሰዱ ዕብራውያን ወጣቶች መካከል ተመርጦ ሦስት ዓመት በከለዳውያን ትምህርት ቤት የከለዳውያንን ጥንቆላ (ኮከበ ቆጣሪ) ሕልም መፍታት፣ ቋንቋ እና ባህላቸውን ከሦስቱ ወጣቶች ጋር በመሆን እንዲያጠኑ በተቃራኒው ደግሞ የራሳቸው የሆነውን የእስራኤልን እምነት እና ባሕል እንዲረሱ በተደረጉበት ጊዜ ዳንኤል እንዲመገቡ የተፈቀዱላቸውን የንጉሡን ምግብ እና መጠጥ ከመብላት እንቢ አለ፤ የአሕዛብ ምግብ እንደሚያረክሰው አስቧልና፡፡ ይልቁንም ቆሎ እየበሉ ይማሩ እንደነበር ትንቢተ ዳንኤል ያስገነዝበናል፡፡

ሰውነታቸው ቅቤን በማጣት ቢነጣም ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸው ኅብረት በጣም ከፍተኛ ነበር፡፡ በጾም መጠንከራቸው በትምህርታቸው ጎበዝ እና በንጉሥ ፊት ሞገስ ያላቸው የሚመረጡ ከመሆን አላገዳቸውም፤ እንዲያውም ከሌሎቹ በላይ ሞገስ እንዲኖራቸው በሀገሪቱ ውስጥ ሥልጣን እንዲያገኙ፣ የተደበቀን ምሥጢር በመግለጥ የበረቱ እንዲሆኑ አደረጋቸው እንጂ፡፡ እግዚአብሔርም በነገር ሁሉ ይረዳቸውና ከጎናቸው ይሆንላቸው እንደነበረ መጽሐፍ ያስገነዝበናል፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው በጾም በመጽናታቸው እና ከኃጢአት ራሳቸውን በመጠበቃቸው ባገኙት ኃይለ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ስለዚህ ወጣቶች (የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች) ስንጾም በትምህርታችን ልንደክም እንደምንችል እያሰብን እግዚአብሔር ከሚሰጠን ኃይል እና ጥበብ እንዳንርቅ ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡

ክርስቲያን መንፈሳዊ ተግባራትን በተመቸው ቀን ብቻ የሚተገብር አይደለም በጊዜውም ያለጊዜውም ጸንቶ የሚገኝ ነው እንጂ፡፡ ጾም ሌሎችን ምግባራት (ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት…) ለመፈጸም ፍጹም ኃይልን የምትሠጥ በጎ ተግባር ናት፡፡ የመንፈሳውያን ኃይል የሆኑትን ትዕግሥትን፣ ቸርነትን፣ በጎነትን፣ ራስን መግዛትንወዘተ ገንዘብ ለማድረግ ጾም ዋና መሣሪያችን ነው እና ገንዘብ እናድርገው፡፡

. ተጋድሎን መፈጸሚያ ነው

በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምንጋደለው ከመንፈሳውያን የክፋት ሠራዊት ጋር እንደሆነ እንዲህ በማለት ተነግሮናልመጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።” (ኤፌ. ፮፥፲፪)፡፡ ለመጋደል የተዘጋጀ ሰው ደግሞ መሣሪያ እንደሚያስፈልገው  ይታወቃል ስለዚህ ጾም ከሁሉ ቀድሞ የሚገኝ ተጋድሎ የመፈጸሚያ መሣሪያ ነው፡፡ በቀንና በሌሊት ከቤተ መቅደስ ሳይለዩ እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ያገለገሉ ቅዱሳን የክፋት ሠራዊትን ድል የማድረግ ኃይልን ተጎናጽፈዋል፡፡ ልባችን በጸጋ እንጂ በምግብ እንዳይጸና ሐዋርያው አስጠንቅቆናል፤ ምግብን አብዝቶ በመብላት እና ለምግብ በማድላት የተጎዳ እንጂ የተጠቀመ እንደሌለ አስተምሮናልና (ዕብ. ፲፫፥፱)፡፡

የተወደዳችሁ ተማሪዎች ተድላና ደስታን በመፈለግ መንግሥተ እግዚአብሔር አትወረስም፡፡ እስኪ ሊቀ ነቢያት ሙሴን እንመልከት ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከክርስቶስ ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መራብን መረጠ፡፡ በዚህ ምክንያት ከሞቀ መኖሪያ ከቤተ መንግሥት ለስደት ተዳረገ፤ ተራበም፤ ተጠማም የሚያገኘውን ዋጋ በዚያ ዘመን ሆኖ ተመልክቷልና (ዕብ. ፲፩፥፳፬፳፭)፡፡ ይህን በማድረጉ ተጎዳ ወይስ ተጠቀመ? በጣም ተጠቀመ እንጂ የተጎዳው አንዳች አልነበረም፡፡ ሙሴ ለዐርባ ቀናት ከምግብ በመከልከል ከእግዚአብሔር ጋር በመነጋገር ሕግጋትን ታቦትን ከአምላከ ቅዱሳን መቀበል የቻለው በጾም በመጋደሉ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ሰማይን እስከ መለጎም የደረሰ ሥልጣንን ማግኘት የቻለው ዐርባ ቀን እና ሌሊት ለመጾም ይከብድብኛል ሰውነቴ ይከሳል ሳይል ሳይፈራ በጾም በጸሎት በመቆሙ ከክፉዎች ጋር ባለመተባበሩ ነው፡፡ ስለዚህ በረጅሙ የክርስትና ጉዙአችን ውስጥ ጾም በጣም ወሳኝ ነገር መሆኑን ማሰብ እንደሚገባ ልንጋደል ይገባል፡፡ የሥጋችን ፈቃድ ለመግዛት በምናደርገው ተጋድሎ ውስጥ ጾም ጉልህ ሚና አለው፡፡ ጾም የነፍስን ቁስል ትፈውሳለች፤ የሥጋንም ፈቃድ ወይም ፍላጎት ዝም ጸጥ ታሰኛለች እና ለተጋድሎ ጠቃሚ መሣሪያ ናት፡፡

. እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመኖር

የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰው ሕያው ሆኖ እንዲኖር ነው፡፡ ማንም በሞት እንዲጠፋ ከገነት ከመንግሥተ ሰማይ እንዲጎድል አይፈልግም፡፡ የሰው ትልቁ ተስፋ መንግሥተ እግዚአብሔርን ወርሶ ዘለዓለማዊ መሆን ነው፡፡ የሕይወት መውጫው ልባችን እንደሆነ መጽሐፍ ይነግረናልአጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና።” (ምሳ. ፬፥፳፫) አዳም አባታችን አትብላ የምትለውን ሕግ በመሻሩ የሥጋ ፈቃዱን በመፈጸም ከፈቃደ እግዚአብሔር ርቆ በእግረ ሞት ተረግጧል፤ እኛም ከዚህ ሕግ ፈቀቅ ብንል የአዳም ዕጣ ሊገጥመን እንደሚችል ጥርጥር የለውም፡፡ ታዲያ ፈቃደ እግዚአብሔር እየፈጸምን ለመኖር ምን ያስፈልገናል? ካልን ራስን መግዛት የምታስችለውን ጾምን ገንዘብ ማድረግ ነው፡፡ (ኢዩ. ፪፥፲፪) በፍጹም ልብ በመጾም ወደ እርሱ እንድንመለስ መማጸኑ እግዚአብሔር የሚወዳት ጾም ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም የሚያስችል ትልቅ ኃይል እንዳላት ያመለክታል፡፡ ጾም በሰው ጥበብ የተጀመረች ሕግ አይደለችም ምን እንደምትጠቅም የሚያውቅ አምላክ ፈቃዱን እንድንፈጽምባት የሠራት ሕግ ናት እንጂ፡፡

በመጀመሪያ ከመጾማችን በፊት ጾም አድካሚ እና ጎጂ ሕግ ነው ብለን ከመሳት ራሳችንን ልንጠብቅ ይገባል፡፡ ይህ ሕግ የፍቅር ሕግ ነው፤ ከአምላካችን ጋር ኅብረት የምናደርግበት የምሕረት ዓይኑ እንድትመለከተን የምታደርግ ሕግ ስለሆነች በጾም ወደ ፈጣሪ መመለስን እንደ መጎዳት ማሰብ ፈጽሞ ስህተትን ያስከትላልና እንጠንቀቅ፡፡ ፈተና እየተፈተንም ቢሆን እያጠናን ልወድቅ እችላለሁ በሚል ፍርሃት አምላክን ከማሳዘን ከመንግሥቱ ከመጉደል መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡

በአጠቃላይ የክርስትና ዋና ዓላማ በእንግድነት በዚህ ዓለም ባለንበት ዘመን ከፈቃደ ሥጋ መራቅ፤ ነፍስና ሥጋን ማንጻትና የእግዚአብሔር ማደሪያ ማድረግ ነው። ይህ ደግሞ በብዙ ድካምና ተጋድሎ የሚሳካ ነው። በመጽሐፍ “. . . ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል።” (ሐዋ. ፲፬፥፳፪) እንደተባለ መንገዱ የተደላደለ ሳይሆን ብዙ ተጋድሎ የሚያስፈልገው መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል። ገዢዋ የሥጋ ፈቃድ የሆነባት ሰውነት ሞት ያገኛታልበገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፥ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘለዓለምን ሕይወት ያጭዳል።” (ገላ. ፮፥፰) እንዲል ሥጋን በጾም ለነፍስ ማስገዛት ሕይወትን ያስገኛል።

እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፤ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ። በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና። ” (ሮሜ. ፰፥ ፲፫፲፬) ጾም ፈጽሞ የሥጋ ሥራን ማስወገጃ፣ ተጋድሎን መፈጸሚያ መንገድ ነው።  “መብል ለሆድ ነው፥ ሆድም ለመብል ነው፤ እግዚአብሔር ግን ይህንም ያንም ያጠፋቸዋል። ሥጋ ግን ለጌታ ነው እንጂ ለዝሙት አይደለም፤ ጌታም ለሥጋ ነው” (፩ኛቆሮ. ፮፥፲፫) ሥጋዊ መብልን በመብላት የሚሠራ ጽድቅ የለም፤ ይልቁንም ብዙ ምግብ ለዝሙት፣ ለትዕቢት የሚያጋልጥ በመሆኑ በጾም ሰውነታችንን ከትዕቢት እንዲሁም ከዝሙት እንጠብቅ። ይህንን ካደረግን ከሆድ ጋር ከመጥፋት ራሳችንን እንታደጋለን። መንፈሳዊ ፍሬን ለማፍራት የምትቀድም ምግባር ጾም ናት ስለዚህ አጥብቀን እንፈልጋት እንያዛትም።የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችምና።” (ሮሜ. ፲፬፥፲፯) በጾም የምናገኛት ተስፋችን ምን እንደምትመስል በታወቀ ጊዜ ከምግብና ከክፋት በመራቅ የምንገባባት መሆኗንስ ተረዳን? ሰው ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ የሚያስፈልገው ጾም እንጂ ምግብ አይደለምመብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም፤ ባንበላም ምንም አይጎድለንም ብንበላም ምንም አይተርፈንም።” (፩ኛቆሮ. ፰፥፰) እንደተባለ። የምግብ ኃይል ለሥጋ ነው የጾም ኃይሏ ግን ለነፍስ ነውየክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑት ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ።” (ገላ. ፭፥፳) የተባለውን እናስተውል።

ይቆየን

 

ጾመ ነቢያት

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሰባት የዐዋጅ አጽዋማትን በቀናት፣ በሳምንታትና በወራት ቀምራ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ እንጠቀምበት ዘንድ ደንግጋ አበርክታለች፡፡ ከእነዚህ አጽዋማት መካከል ደግሞ ጾመ ነቢያት አንዱ ሲሆን ኦርቶዶክሳውያን ከኅዳር ፲፭ እስከ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ዋዜማ ድረስ የምንጾመው ጾም ነው፡፡  

እግዚአብሔር ለአዳም አባታችን በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ይህንን ዓለም ያድን ዘንድ የሰውን ሥጋ ለብሶ እንደሚወለድ ነቢያት በትንቢት መነጽርነት ተመልክተው ተናግረዋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፣ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፤ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” (ኢሳ. ፯፥፥፲፬) እንዲል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩከአጥቢያ ኮከብ አስቀድሞ ከሆድ ወለድሁህተብሎ እንደተጻፈው፡፡ (መዝ. ፻፱፥፫) በተጨማሪምእነሆ በኤፍራታ ሰማነው፤ ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው፤ እንግዲህስ ወደ እግዚአብሔር ማደሪያዎች እንገባለን፤ የጌታችን እግሮቹ በሚቆሙበት ቦታ እንሰግዳለን” (መዝ. ፻፴፩፥፮) በማለትይወርዳል፣ ይወለዳልየሚለውን የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይህን ዓለም ለማዳን በሥጋ መምጣት ተናግረዋል፡፡ ነቢያት በዚህ ብቻ ሳያበቁ ስለ ስደቱ፣ ስለ ጥምቀቱ፣ ወንጌልን ስለመስበኩ፣ መከራ ስለ መቀበሉ፣ ስለ ሞቱ፣ ስለ ትንሣኤው፣ ዕርገቱና ዳግም ምጽዓቱ በትንቢት ተናግረዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነቢያት የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መወለድ እየናፈቁ ጾመውታልና ጾመ ነቢያት ተብሏል፡፡

የነቢያት ትንቢት ፍጻሜውን አግኝቶ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜም የአዳም ተስፋው ተፈጽሟልናጾመ አዳምእየተባለም ይጠራል፡፡ የጾሙ መጨረሻም በዓለ ልደት በመሆኑጾመ ልደትይባላል፡፡ የነቢያት ትንቢት ተፈጽሞ ጨለማውን ዓለም በወንጌል ብርሃንነት (በስብከት) አጣፍጧልናጾመ ስብከትተብሎ ይጠራል፡፡

እንደዚሁም ሐዋርያት በዓለ ልደቱን እንዴት ዝም ብለን እናከብረዋለን? ነቢያት አባቶቻችንይወርዳል ይወለዳልብለው በተስፋ እየናፈቁ ጾመውታል፤ በዓለ ትንሣኤውን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብረዋለን፤ በዓለ ልደቱንም ጾመን በረከት እናገኝበታለን ሲሉ ጾመውታልናጾመ ሐዋርያትይባላል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን እንደምትፀንስ ካበሠራት በኋላ “ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?” በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ ጾማዋለችና ይህ ጾምጾመ ማርያምእየተባለም ይጠራል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በነቢያት ጾም ነቢያት፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ሐዋርያት፣ ጻድቃን ሰማዕታት ጾመው በረከት አግኝተውበታልና እኛ ምእመናንም በረከትን እናገኝ ዘንድ መጾም እንደሚገባን የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ ጾመን፣ ጸልየን የበረከቱ ተሳታፊዎች ያድርገን፡፡ አሜን፡፡  

ምንጭ፡

ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡

ጾምና ምጽዋት፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯፶፡፡

 

በዓታ ለማርያም

ንጽሕተ ንጹሐን፣ ቅድስተ ቅዱሳን፣ ከተመረጡ የተመረጠች፣ ከተለዩ የተለየች፣ ከተከበሩ የተከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእናቷ ከቅድስት ሐናና ከአባቷ ቅዱስ ኢያቄም በእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ ከተወለደችበት ዕለት ግንቦት ቀን ጀምሮ በወላጆቿ ቤት ለሦስት ዓመት ከኖረች በኋላ ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ታኅሣሥ ቀን ‹‹በዓታ ለማርያም›› በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡

ኢያቄምና ሐና የተሳሉትን ስእለታቸው አስታውሰው ወስደው ለቤተ እግዚአብሔር ሲሰጧትም ካህኑ ዘካርያስ ስለምግቧ ተጨነቀ፤ ሕዝቡንም ሰብስቦ ሳለ መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፤ ዘካርያስ ለእርሱ የመጣ ሀብት መስሎት ታጥቆ እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ ከስምዖን ጀምሮ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም በተራ ቢሞክሩ በተመሳሳይ መልኩ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ ‹‹ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ›› ብለው ሐና እና ኢያቄም እንዲቀርቡ አደረጓቸው፤ ነገር ግን ለእነርሱም ራቀባቸው፤ ዘካርያስም ሐናን ‹‹እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ›› አላት፤ በዚያም ጊዜ ቅድስት ማርያም እናቷን ስትከተል መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መገባት፤ ከዚያም በክብር ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱና ሕዝቡም ‹‹የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር›› ብለው ወደ ቤተ መቅደስ አስገቧት፡፡

ለ፲፪ዓመታትም ቅድስት ድንግል ማርያም ሰማያዊ ኅብስትና መጠጥ እየተመገበች በቤተ መቅደስ ኖረች፡፡ በ፲፭ ዓመቷ ግን ለአቅመ ሔዋን በመድረሷ ከቤተ መቅደስ ትውጣልን በማለት አይሁድ በጠላትነት ተነሡባት፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ይህን ሰምቶ እመቤታችንን እንዲህ ብሎ ጠየቃት፤ « ወለተ እስራኤል እፎ ትፈቅዲ ትንበሪ፤ ልጄ እንደምን ሆነሽ ልትኖሪ ትወጂያለሽእርሷም «ከእግዚአብሐር በታች ያለኸኝ አባት አንተ ነህ፤ በዚያውም ላይ እናት አባቴ አደራ ያሉህ አንተን ነው፤ ወደ እግዚአብሔር አመልክትልኝ» አለችው፡፡ ካህኑ ዘካርያስም በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ እንዲህ ብሎ አዘዘው፤ «ከነገደ ይሁዳ ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን በትራቸውን ሰብስበህ በቀዳማይ ሰዓተ ሌሊት ከቤተ መቅደስ አግብተህ ስትጸልይ እደር፤ በቀዳማይ ሰዓተ መዓልት አውጣው፤ ምልክትም አሳይህአለው፡፡» እርሱም እንዳለው አድርጎ በማግሥቱ በትሮቹን አውጥተው ቢያዩ የአረጋዊው ዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩ ጫፍ ላይ « ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ፥ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት» የሚል ጽሑፍ አገኙ፤ ርግብም መጥታ በራሱ ላይ ዐረፈች፤ ስለሆነም ዮሴፍ እንዲጠብቃት ተወሰነ፡፡

ከዚህም በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከቤተ መቅደስ ወጥታ እስከተሰደደችበት ወራት ድረስ ዮሴፍ ቤት ኖረች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልመኗ ክብሯ በሁላችን ላይ ይደርብን፤ አሜን፡፡

 

የዳረጎት ዕጣዎች

ማኅበረ ቅዱሳን ከግንቦት ፩ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ጀምሮ ሲያሠራጨው የነበረው የገቢ ማሰባሰቢያ ትኬት  ኅዳር ፳፩ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም ዕጣ ማውጣቱ ይታወቃለል፡፡ በዚህም መሠረት ፳፩ የዳረጎት ዕጣዎች የወጡ ሲሆን ዐሥር የዕጣዎች እያንዳንዳቸው የሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ፤ እንዲሁም ዐሥራ አንድ ዕጣዎች እያንዳንዳቸው መዝሙረ ዳዊት የሚያስገኙ ሆነው ወጥተዋል፡፡  

በዚህም መሠረት የሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስገኙት ዕጣዎች፡-

  • 373427
  • 360509
  • 345974
  • 249715
  • 263391
  • 435703
  • 320085
  • 394074
  • 315800
  • 232590

ዐሥራ አንድ የመዝሙረ ዳዊት የጸሎት መጽሐፍ የሚያስገኙት ዕጣዎች፡-

  • 374223
  • 354749
  • 247657
  • 265287
  • 317331
  • 435060
  • 319033
  • 291453
  • 179959
  • 259285
  • 244216 ሆነው ወጥተዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የባለ ዕድለኞች ዕጣ ቁጥሮችን ይፋ አደረገ

ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎትን ለማጠናከር ይረዳው ዘንድ “ዘመኑን የዋጀ ንቁ ትውልድ ለቤተ ክርስቲያን” በሚል መሪ ቃል ለአባላት፣ ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና አገልግሎቱን ለሚደግፉ ምእመናን ሲያሠራጭ የቆየው ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም፣ ወደ ግብጽና ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝትን ጨምሮ ሌሎችንም ዕድሎችን የሚያስገኙት የበረከት የዕጣ ቁጥሮች በቴክኖሎጂ በታገዘ የዕጣ አወጣጥ መርሐ ግብር ታዛቢዎችና ምእመናን በተገኙበት ኅዳር ፳፩ ቀን ፳፳፻፲፰ ዓ.ም ይፋ አደረገ፡፡  

በዕጣ አወጣጥ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ መምህር ዋሲሁን በላይ ባስተላለፉት መልእክት “ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በተሻለ ጥራትና አቅም ለማስተማር ብቻውን ሳይሆን የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ፣ የሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የመምህራንና የምእመናን ትብብርና ድጋፍ ሳይለየው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በተሻለ ጥራትና አቅም አገልግሎቱን እየሰጠ ይገኛል” በማለት የገለጹ ሲሆን የበረከት ዕጣ ትኬቱን በማሠራጨት ሂደት ውስጥ የተሳተፉትን ሁሉ አመስግነዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ አበበ በዳዳ የበረከት ዕጣ ትኬቱ የተዘጋጀበት ምክንያትና ሂደቱን በተመለከተ ባስተላለፉት መልእክት “ማኅበረ ቅዱሳን ከ፲፱፻፹፬ ዓ.ም ጀርሮ በቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠው ፈቃድና ኃላፊነት መሠረት  የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ለማስተማር መምህራንን በመመደብ፣ መማሪያ ቦታን በማዘጋጀት፣ በንስሓ አባቶች አማካይነት ሕይወታቸውን በመንፈሳዊ መንገድ እንዲመሩ በማድረግ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ኦርቶዶክሰውያን ተማሪዎችን በማፍራት አስመርቋል፡፡ “በዚህም አገልግሎት ተማሪዎች ለራሳቸው፣ ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ አገልግሎት እያበረከቱ ይገኛሉ፡፡” ብለዋል፡፡

አቶ አበበ አያይዘውም “ማኅበረ ቅዱሳን ከ፲፱፩፺፮ ዓ.ም ጀምሮም ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ሲያስተምር በየጊዜው የሚታዩ ክፍተቶችን በማረም በ፳፻፮ ዓ.ም በዓለማችን፣ በሀገራችንና በቤተ ክርስቲያን በሚታዩ ተለዋዋጭ ሁኔታዎች፣ የሰ/ት ት/ቤቶች ከ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ሥርዓተ ትምህርት መዘጋጀት፣ ማኅበረ ቅዱሳን ከ፳፻፲፮ ዓ.ም የተቋማዊ ለውጥ ትግበራ መጀመርና የመንግሥት የትምህርት ፖሊሲ መቀያየር ከግምት ውስጥ በማስገባት ከዐሥር ዓመታት በኋላ በ፳፻፲፯ ዓ.ም ለግቢ ጉባኤያት ሲሰጠው የነበረውን ሥርዓተ ትምህርት ከግምት ውስጥ በማስገባት መከለስ ችሏል” ሲሉ ገልጸዋል፡፡

“እነዚህም ምክንያቶችን መሠረት በማድረግ ፲፬ የትምህርት ዓይነቶች የተዘጋጁ ሲሆን ለኅትመት፣ የመምህራንን አቅም፣ ጥራትና ቁጥር ለማሳደግ፣ የመማሪያ ቦታ ችግሮችን ለመቅረፍና የሥልጠና መስጫ መእከል ለመገንባት ታስቦ የበረከት ዕጣው ተዘጋጅቷል” በማለት አብራርተዋል፡፡

በበረከት ዕጣ ትኬቱ አቅማቸውን ሁሉ በመጠቀም ድጋፍ ላደረጉና በማሠራጨት ለተባበሩት አካላት ሁሉ ምስጋና በማቅረብ የዕጣ መውጣት መርሐ ግብሩ እንዲጀመር አድርገዋል፡፡ በዚህም መሠረት፡-

፩ኛ ዕጣ፡- 409652፡- ወደ ኢየሩሳሌሌም ገዳማት ጉዞ ለ፯ ቀናት፣  

፪ኛ ዕጣ፡- 309903፡- ወደ ግብጽ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝት ለ፯ ቀናት፣

፫ኛ ዕጣ፡- 076840፡- ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት ወደ አንዱ ከአንድ ቤተሰብ ጋር መንፈሳዊ ጉብኝነት በአውሮፕላን ለ፭ ቀናት፣

፬ኛ ዕጣ፡- 366930፡- ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝት ከሁለት ቤተሰብ ጋር በየብስ ትራንስፖርት ለ፯ ቀናት፣

፭ኛ ዕጣ፡- 160582፡- ላፕቶፕ ኮምፐዩተር core i7 10Th G የሚያስገኘው የዕጣ ቁጥር፣

፮ኛ ዕጣ፡- 201414፡- ላፕቶፕ ኮምፒዩተር core i5 የሚያስገኘው የዕጣ ቁጥር፣

፯ኛ ዕጣ፡- 478450፡- ሳምሰንግ ታብሌት ጋላክሲ (Samsung Galaxy tablet A8 10.5) ሆነው ወጥተዋል፡፡

ኅዳር ጽዮን

በዓለ ሢመቱ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል

በዲ/ን አብርሃም

ኅዳር ፲፪ ቀን ንዑድ ክቡር የሆነ ለፍጥረቱ ሁሉ የሚማልድ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል የተሾመበት ዕለት ነው። የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍት “ኅዳር ፲፪ በዚህች ቀን ለሰው ወገን የሚያዝንና የሚራራ በእግዚአብሔር ጌትነት ፊት ሁል ጊዜ በመቆም ለፍጥረቱ ሁሉ የሚማልድ የመላእክት አለቃቸው ለሆነ ለቅዱስ ሚካኤል የበዓለ ሢመቱ መታሰቢያ ነው።” (መጽሐፈ ስንክሳር ኅዳር ፲፪፤ ድርሳነ ሚካኤል ዘኅዳር) በማለት ይገልጻሉ፡፡

ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‘ሚ’- ‘መኑ’፣ ‘ካ’- ‘ከመ’፣ ‘ኤል’- ‘አምላክ’ ማለት ሲሆን በአንድነት ሲነበብ “መኑ ከመ አምላክ፤ እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?” ማለት ነው። እግዚአብሔር መልእክትን በፈጠረ ጊዜ ሳጥናኤልን የመላእክት ሁሉ አለቃቸው አድርጎ ሹሞት ነበር። ነገር ግን ሳጥናኤል ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ክብር ትቶ አምላክነትን በመሻቱ በትዕቢቱ ምክንያት ሥልጣኑን ገፍፎ ወደ ጥልቁ ጥሎታል፤ በቦታውም ቅዱስ ሚካኤልን ሹሞታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህን ምክንያት በማድረግ ኅዳር ፲፪ ቀን በየዓመቱ በዓለ ሢመቱን ታክብራለች።

ደጉ እና ሩኅሩኁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በስሙ ለተማጸንን ሁሉ ከእግዚአብሔር የሚያማልደን ምሕረትን የሚያሰጠን መልአክ ነው ”ተውህቦ ምሕረት ለሚካኤል” እንዲል (ሥርዓተ ቅዳሴ)። ቅዱስ ሚካኤል ለፍጥረታት ሁሉ የሚራዳና የሚያዝን በእግዚአብሔር ፊት የሚቆምልን የምሕረትና የሰላም መልአክ ነው። “በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል” (ዳን. ፲፪፥፩) ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤል ‎የቅዱስ ሚካኤልን ክብር ሲገልጥ ይህንን ብሎ ብቻ አልቀረም “ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ” በማለት እኛ የአዳም ልጆች ዲያብሎስ ባዘጋጀልን መሰናክል እንዳንወድቅ የሚረዳን መልአክ እንደሆነ ይናገራል፡፡ (ዳን. ፲፥፲፫)

“ቅዱስ ሚካኤል ሆይ የያሬድ ልጅ ሄኖክ እንደጻፈው። ከልዑል ስም አጠራር ጋር ለተባበረ ስም አጠራርህ ሰላም እላለሁ። የእግዚአብሔር የምክሩ አበጋዝ ሆይ የተቸገሩትን የተጨነቁትን ዘወትር እንደምትረዳቸው ሁሉ እኔንም ለመርዳት ክንፍህን ዘርግተህ ፈጥነህ ድረስልኝ።” በማለት የቅዱስ ሚካኤልን ተራዳኢነት ይገልጻል፡፡ (መልክአ ሚካኤል)

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት የቅዱስ ሚካኤልንና የሌሎች መላእክትን ክብርና አገልግሎት ሲገልጥ “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።”‎ (መዝ. ፴፫፥፯) እንዲል ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን በሚፈሩ ሰዎች ዙሪያ ሁል ጊዜ ይከባሉ፤ ከሰይጣን ፈተና፣ ከረኃብ፣ ከችግር፣ ከመከራ ሁሉ ያድኑናል። ማዳናቸውም የክርስቶስን የማዳን ሥራ የሚተካከል አይደለም፤ እርሱ በሰጣቸው ጸጋ ከእርሱ ዘንድ ይቅርታንና ምሕረትን በማሰጠት የሚያድኑን ናቸው እንጂ።

ቅዱስ ሚካኤል አርምሞንና ትዕግሥትን የሚያስተምረን መልአክ ነው። “የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እንኳን ስለ ሙሴ ሥጋ ከሰይጣን ጋር በተከራከረ ጊዜ የስድብ ቃልን ሊናገር አልደፈረም፤ ‘እግዚአብሔር ይገስጽህ’ አለው እንጂ” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ (ይሁዳ ፩፥፱)

የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤል ጥበቃው አይለየን! ከበዓሉ በረከት ይክፈለን!

ወርኀ ጽጌ

ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ቀን ድረስ ያለው ወቅት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ዘመነ ጽጌ ወይም ወርኀ ጽጌ ተብሎ ይጠራል፡፡ ክረምቱ አልፎ ሰማዩ የሚጠራበት፣ የምድር አበቦች የሚፈኩበትና የሚደምቁበት፣ ሜዳውና ሸንተረሩ ልምላሜ የሚላበሱበት፣ ወንዞች የሚጠሩበትና ለፍጥረታት ሁሉ ተስማሚ አየር የሚነፍስበት ጊዜ ነው፡፡   

ይህ ወቅት ሄሮድስ ከእኔ ሌላ ንጉሥ እስራኤልን ማን ሊገዛ ይችላል? በሚል በይሁዳ ክፍል በቤተ ልሔም በከብቶች ግርግም የተወለደውን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመግደል መነሣቱን የምናስብብት ጊዜ ነው፡፡ የእግዚአብሔር መልአክም በሕልም ለአረጋዊው ዮሴፍ ተገልጦ “ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይሻዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ምድረ ግብጽ ሽሽ፤ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ኑር” በማለት ሲነግረው ሕፃኑና እናቱን ይዞ ሰሎሜን ትረዳቸው ዘንድ አስከትሎ ወደ ግብጽ ሸሸ፡፡

በነቢያት የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ “የይሁዳ ምድር አንቺ ቤተልሔም ከይሁዳ አለቆች ከቶ አታንሺም፤ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ ንጉሥ ከአንቺ ይወጣልና” ተብሎ እንደተጻፈ ሄሮድስ በቅናት ተነሣስቶ በቤተ ልሔምና በአውራጃዎችዋ የተወለዱትን ሁለት ዓመትና ከዚያም በታች ዕድሜ ያላቸውን ፻፵፬ ሺህ ሕፃናትን አስገደለ፤ ዋይታና ጩኸትም ሆነ፡፡ በነቢዩ ኤርምያስ የተነገረው ትንቢትም ተፈጸመ፡፡ “ራሔል ስለ ልጆችዋ ስታለቅስ ብዙ ልቅሶና ዋይታ በራማ ተሰማ፤ መጽናናትንም እንቢ አለች፤ ልጆችዋ የሉምና” (ማቴ. ፪፥፲፰) ተብሎ እንደተጻፈው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችን ፀንሳ በነበረች ጊዜ ለአረጋዊው ዮሴፍ አንዳንድ ጊዜ ቀይ የነበረው መልኳ ተለውጦ እንደ ሮማን አበባ ቀይ፣ ቀይ የነበረው ጸዓዳ ነጭ አበባ፣ ነጭ የነበረው እንደ ጽጌረዳ ቀይ ሲሆንና የሚያውቀው መልኳ ሲለዋወጥበት ዮሴፍ እየደነገጠ እርሷ መሆኗን “ማርያም” እያለ ያረጋግጥ ነበር፡፡ (ነገረ ማርያም) ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ “የበኩር ልጇን እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም” ያለውን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሲተረጉመው “መልኳ እንደ ጽጌረዳና እንደ ሮማን አበባ ይለዋወጥበት ስለነበር በአንድ ዓይነት መልክ አላወቃትም” ብሏል፡፡ (ማቴ. ፩፥፳፭) ያንን ለማውሳት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ያለው ወቅት ወርኀ ጽጌ ተባለ፡፡

የእመቤታችን ወደ ግብፅ ሀገራችን ኢትዮጵያ መሰደድ

ጌታችን ሁለት ዓመት ሲሞላው ሄሮድስ ሊገለው እንደፈለገ የእግዚአብሔር መልአክ ለአረጋዊው ዮሴፍ ከተናገረው በኋላ ወደ ግብፅ ሲሰደዱ በርካታ መከራዎችን አስተናግደዋል፡፡ የቀን ሐሩር፣ የሌሊት ቊር እየተፈራረቁባቸው፣ እሾሁ እየወጋቸው፣ እንቅፋቱ እየመታቸው፣ መውጫና መግቢያው በማይታወቅ በረሃ ውስጥ ብዙ ተሰቃይተዋል፡፡

በግብጽ በረሃ ሲጓዙም እመቤታችን ወደ ትዕማን ቤት በሄደች ጊዜ የቤቱ እመቤት ስታያት “ከየት መጣሽ?” ብላ ጠየቀቻት፤ እመቤታችንም “ከይሁዳ ምድር የተሰደድኩ ስደተኛ ነኝ” አለች፡፡ “አንቺ ሴት ደረቅ ነሽ መሰለኝ፤ በድርቅናሽ ቤትሽን ትተሽ ትዞርያለሽ፤ እንዳንቺ ያለች ቆንጆ ሴት ከአዳራሽ ወደ ዕልፍኝ ይላል እንጂ ሀገሩን ትቶ ሀገር ለሀገር አይንከራተትም” ብላ ተተናኮለቻት፡፡ (ነገረ ማርያም) ዮሴፍም “ለለማኝ ቢኖር ይሰጡታል፤ ባይኖር ደግሞ ካለበት ያድርስህ ይባላል እንጂ እንዲህ እንደ ፍላጻ ልብ የሚወጋ ነገር ምን ያናግርሻል” ብሎ በመለሰላት ጊዜ ኮቲባ የተባለችው የእመቤቲቱ አገልጋይ “ይህ ሽማግሌ ደፍሮ እመቤቴን እንዲህ ይመልስላታል?” ብላ ዮሴፍን በጥፊ ቃጥታ ሕፃኑን ደግሞ ነጥቃ ወደ መሬት ጣለችው፡፡ ሕፃኑም ምርር ብሎ ሲያለቅስ እመቤታችን እርሱን ተከትላ ምርር ብላ አለቀሰች፤ ልታነሣውም በምትሞክርበት ጊዜ ዮሴፍ “ተይው፤ አምላክነቱን ይገለጽ” አላት፡፡ ትዕማንን ከእነ ገረድዋ መሬት ተከፍቶ ዋጣቸው፡፡

ከበረሃውም አልፈው በየዱሩ ከአንዱ መከራ ወደ ሌላው መከራ እየተሸጋገሩ ከቆዩ በኋላ ዕረፍትን ያገኙት ወደ ኢትዮጵያ ከደረሱ በኋላ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች በተዘዋወሩበት ሁሉ ሕዝቡ በእንግድነት እየተቀበለ አስተናግዷቸዋል፤ በዚህም ምክንያት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኢትዮጵያን የአሥራት ሀገር አድርጎ ሰጥቷታል፡፡   

ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ከተፈጸመ በኋላ ጊዜው ሲደርስ ሲያሳድዳቸው የነበረው ሄሮድስ በመሞቱ ለዮሴፍ መልአኩ በሕልም ተገልጦ “የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሙተዋልና ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ” (ማቴ.፪፥፳) አለው፡፡ ዮሴፍም የእግዚአብሔር መልአክ እንደነገረው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንና ልጇን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከሰሎሜ ጋር ይዞ ወደ ገሊላ አውራጃ ሄደ፡፡

አባቶቻችን ይህንን መሠረት አድርገው የእመቤታችንን ስደት በማሰብ በወርኀ ጽጌ በየሳምንቱ ቅዳሜ ለእሑድ ዋዜማ ሌሊት በማሕሌት “አዘክሪ ድንግል ረኀበ ወጽምዐ፣ ድንግል ሆይ ረኀቡንና ጥሙን አሳስቢ” እያልን ከአባቶቻችን ጋር እንዘምራለን፣ ጊዜውንም እናስባለን፡፡ በርካታ ምእመናንም በዚህ ወቅት የእመቤታችንን ስደት በማሰብ ይጾማሉ፣ ይጸልያሉ፡፡

አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ “አዘክሪ ድንግል ንግደቶ ዘምስሌኪ እንዘ ትጐይዪ ምስሌሁ እምሀገር ለሀገር በመዋዕለ ሄሮድስ ርጉም አዘክሪ ድንግል አንብዐ መሪረ ዘውኅዘ እምአዕይንትኪ ወወረደ ዲበ ገጸ ፍቁር ወልድኪ አዘክሪ ድንግል ረኀበ ወጽምዐ ምንዳቤ ወኀዘነ ወኵሎ ዐፀባ ዘበጽሐኪ ምስሌሁ፤ ርጉም ሔሮድስ በነገሠበት ወራት ከአንቺ ጋር ከአንዱ ሀገር ወደ አንዱ ሀገር የተሰደደውን መሰደድ አሳስቢልን፤ በፊትሽና በልጅሽ ፊት የወረደውን መሪር ዕንባ አሳስቢልን፤ ረኀቡን ጥሙን ችግሩንና ኀዘኑን ያገኘሽንም ልዩ ልዩ መከራ አሳስቢልን” (ቅዳሴ ማርያም) ሲል ያዘክራል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በዓለ መስቀል

በመ/ሰላምቀሲስደጀኔሺፈራው (ከአሜሪካ)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመስቀልን በዓል የምታከብረው መስከረም ፲፯ እና መጋቢት ፲ ቀን ነው። እነዚህም አይሁድ በክፋት ቀብረው ሠውረውት የነበረውን መስቀል ለማግኘት ቁፋሮ የተጀመረበት እና መስቀሉ የተገኘበት ዕለታት ናቸው። ክቡር መስቀሉ ከክርስቲያኖች ተሰውሮ የኖረው ለሦስት መቶ ዓመታት ነው።

ክቡር መስቀሉ እንዴት ሊጠፋ ቻለ?

መስከረም ፲፮ እና ፲፯ የሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳር፦ በክፋት የተመሉ አይሁድ፥ በጌታ መስቀል እና መቃብር ምክንያት ይፈጸሙ የነበሩትን አያሌ ተአምራት አይተው በምቀኝነት መነሣሣታቸውን ይተርካል። አይሁድ በኢየሩሳሌምና በአካባቢዋ እስከ ፷፬ ዓ.ም ድረስ ምንም ኃይል አልነበራቸውም። ከ፷፬ ዓ.ም በኋላ ግን ራሳቸውን ከሮማውያን ቅኝ አገዛዝ ነፃ ለማውጣት በጀመሩት ዓመጽ ኢየሩሳሌምን ሙሉ በሙሉ ተቈጣጠሩ። በዚህን ጊዜ ክርስቲያኖቹን ወደ ጌታ መስቀል እና መቃብር እንዳይቀርቡ ከልክለው ቦታውን የቆሻሻ መድፊያ አደረጉት። ከብዙ ጊዜ በኋላ ሥፍራው ትልቅ ጉብታ ሆኖ ከቦታው ጋር ተመሳሳለ። ከዚህም ጋር እስራኤል በየጊዜው ይማርኩ ስለነበር፥ ከምርኮ ሲመለሱም የከተማዪቱ መልክ ስለሚለዋወጥባቸው መስቀሉ የተቀበረበትን ትክክለኛ ጉብታ መለየት አልተቻለም።

በተለይም ከ፻፴፪ – ፻፴፭ ዓ.ም በተደረገው ጦርነት ኢየሩሳሌም ፈጽማ ጠፍታ ነበር። ዳግመኛም ንጉሥ ሐድርያን በ፻፴፭ ዓ.ም. ኢየሩሳሌምን በአዲስ ፕላን በመሥራቱና በጎልጎታ የቬነስን መቅደስ በመገንባቱ ክርስቲያኖቹ ምንም ማድረግ አልተቻላቸውም ነበር። ያን ጊዜ ጎልጎታ ከከተማዋ ውጪ ነበር፥ ዛሬ ግን በአሮጌዋ የኢየሩሳሌም ከተማ ክልል ይገኛል።

መስቀሉ እንዴት ሊገኝ ቻለ?

ክቡር መስቀሉን ፈልጋ ያገኘችው የንጉሥ ቆስጠንጢኖስ እናት ንግሥት ዕሌኒ ናት። ቆስጠንጢኖስ ለክርስቲያኖች ሙሉ ነፃነት የሰጠ ደገኛው የሮም ንጉሥ ነበር። ከዚያ በፊት ምንም ነፃነት አልነበራቸውም።

ቆስጠንጢኖስ ለክርስቲያኖች የሰጣቸው መብት፡-

፩ኛ. ቤተ ክርስቲያንን ከግብር ነፃ አደረጋት።

፪ኛ፦ከመንግሥት ገቢ ለቤተ ክርስቲያን የተወሰነ ድርሻ ሰጣት።
፫ኛ፦ ዕለተ እሑድ የክርስቲያኖች የበዓል ቀን በመሆኗ በግዛቱ ሥራ እንዳይሠራ በ፫፻፳፩ ዓ.ም አወጀ።
፬ኛ፦ ለቤተ ክርስቲያን ኑዛዜ የመቀበልና ውርስ የመውረስ መብት ሰጣት።
፭ኛ በክርስቲያኖች መካከል ለሚፈጠሩ አንዳንድ አለመግባባት፥ ወንጀል ነክ ላልሆነ ጉዳይ ለኤጲስ ቆጳሳት የዳኝነት ሥልጣን ሰጣቸው።

፮ኛ፦ክርስትና የሀገሩ ብሔራዊ ሃይማኖት እንዲሆን አደረገ።

በአጠቃላይ ቤተ ክርስቲያን የወንጌልን የመዳን መልእክት እያወጀች ሐዋርያዊ ጉዞዋን እንድትቀጥል ያደረገ ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ ነው። ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ይህን ያደረገበት ምክንያትም በመስቀል ምልክት የተደረገለት ተአምር ነበር። ይኸውም የሮምን የምዕራቡን ክፍል ይገዛ የነበረው ማክሴንዲዮስ የጦር ኃይሉን ባዘመተበተት ጊዜ፥ እርሱም በበኩሉ «ምታ ነጋሪት፥ ክተት ሠራዊት» ብሎ ለጦርነት ተዘጋጀ። ገና በዝግጅት ላይ እንዳለም፦ «በዚህ ድል ታደርጋለህ፤» የሚል በመስቀል ቅርጽ የተጻፈ ጽሑፍ በጠፈረ ሰማይ አየ። በዚህን ጊዜ፦ ሠራዊቱ በፈረሱ አንገት፥ በጋሻው እምብርት መስቀላዊ ቅርጽ እንዲያደርግ አወጀ።
ሮምን ሙሉ በሙሉ ጠቅልሎ መግዛት የጀመረው ከዚህ በኋላ ነበር። ከዚያ በፊት ለአርባ ዓመታት ለአራት ተከፍላ በኋላም ለሁለት ተከፍላ ትተዳደር ነበር።

ጦርነቱም በመስቀሉ ኃይል ጠላቶቹን ድል አድርጎ ተመለሰ እናቱ ንግሥት ዕሌኒ በልጇ ዘመን የተገኘውን የክርስትና ነፃነት ተጠቅማ በ፫፻፳፯ ዓ.ም. ክቡር መስቀሉን ፍለጋ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች። በዚያም ጉብታ የሆነውን ሥፍራ ሁሉ በማስቆፈር ብዙ ብትደክምም መስቀሉን ለማግኘት አልቻለችም። በዚህን ጊዜ ኪራኮስ የተባለው አረጋዊ፦ «ደመራ አስደምረሽ፥ ዕጣን አፍስሰሽ፥ ብታቀጣጥዪው ጢሱ ይመራሻል፤» ባላት መሠረት ሳትጠራጠር አደረገችው። የዕጣኑ ጢስ መስቀሉ ከተቀበረበት ጉብታ ላይ እንደ ቀስተ ደመና ተተክሎ በጣት ጠቅሶ የማሳየት ያህል አመለከታት።

ቁፋሮውም መስከረም ፲፯ ተጀምሮ መጋቢት ፲ ተፈጸመ። የተገኙት ሦስት መስቀሎች ስለነበሩ የክርስቶስን መስቀል በተአምራቱ ለዩት። ዕውር አበራ፥ አንካሳ አረታ፥ ለምጽ አነጻ፥ ሙት አስነሣ። ንግሥቲቱም ያን ተአምራትን የሚያደርግ ቅዱስ መስቀል የከበረ ቤተ ክርስቲያን አሠርታ በክብር እንዲቀመጥ አደረገች።

መስቀል፤ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ተላልፎ በመሰጠት ቅዱስ ሥጋውን የቆረሰበት፥ ክቡር ደሙንም ያፈሰሰበት ነውና ሃይማኖታዊ ትርጉም አለው። መሰቀል ድኅነታችን የተፈጸመበት (መዳናችን የተረጋገጠበት) ነው «ኢየሱስም ሆምጣጣውን ከተቀበለ በኋላ ተፈጸመ፥ አለ»ይላል (ዮሐ፲፱፥፴) በመስቀል ላይ የተፈጸመው ድኅነታችን (መዳናችን) ነው። ይኸውም የዕለት ፅንስ ሆኖ በማኅፀነ ድንግል ማርያም የጀመረውን የማዳን ሥራ ነው (ሉቃ. ፩፥፴፩)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ፦ «በእርሱም እንደ ቸርነቱ ብዛት በደሙ ድኅነትን አገኘን፥ ኃጢአታችንም ተሠረየልን» ብሏል። መድኃኒት ከድንግል ማርያም መወለዱን ለእረኞች አስቀድመው የሰበኩት ቅዱሳን መላእክት ናቸው (ሉቃ. ፪፥፲፩) መርገመ ሥጋ መርገም ነፍስን የተወገደበት ቅዱስ መስቀል መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የተወገደበት ነው አዳምና ሔዋንሕገ እግዚአብሔርን በመተላለፋቸው የወደቀባቸው የሥጋና የነፍስ መርገም ለሰው ልጅ በጠቅላላ ተርፎት ነበር። «ነገር ግን በአዳም ኃጢአት ምክንያት ከአዳም እስከ ሙሴ (እስከ ክርስቶስ) የበደሉትንም ያልበደ ሉትንም ሞት ገዛቸው።» ይላል( ሮሜ ፭፥፲፬) ሙሴ ለክርስቶስ ምሳሌ ነው። በኦሪቱ እንደተጻፈው በእንጨት ተሰቅለው የሚሞቱ ርጉማን ነበሩ( ዘዳ.፳፩፥ ፳፫)
ይህንም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፦ «በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው፥ ተብሎ ተጽፎአልና፤ ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ (መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን ያመጣብንን ኃጢአት ለመደምሰስ ተላልፎ በመሠዋት) ከሕግ እርግማን ዋጀን።» በማለት ገልጦታል (ገላ. ፫፥፲፫) ቅዱስ ጴጥሮስም፦ «እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ።» ብሏል (፩ኛ ጴጥ. ፪፥፳፬)

ዲያብሎስ የተሸነፈበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል፤ ዲያብሎስ የተሸነፈበት ነው ጥንተ ጠላታችንን (ገነትን ያህል ርስት፥ እግዚአብሔርን ያህል አባት ያሳጣንን ዲያብሎስን) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድል ያደረገልን በመስቀሉ ነው።«ጥልን በመስቀሉ ገደል፤» ይላልና። (ኤፌ. ፪፥፲፮) ጥል የተባለው ለሰውና ለእግዚአብሔር መጣላት ምክንያት የሆነ ዲያብሎስ ነው። እኛም በኃይለ መስቀሉ ድል እያደረግነው የምንኖር ሆነናል።

የጥል ግድግዳ የፈረሰበት ቅዱስ መስቀል

መሰቀል የጥል ግድግዳ የፈረሰበት ነው፤የጥል ግድግዳ የተባለው ኃጢአት ነው። እርሱም ሰውና እግዚአብሔ ርን ለያይቷቸው ኖሯል። «በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሠውሮታል።» ይላል (ኢሳ. ፶፱፥፪) ይህ ከእግዚአብሔር ለያይቶን እግዚአብሔርን ሰውሮብን የኖረ የጥል ግድግዳ (በዲያብሎስ ምክር የተሠራ ኃጢአት) የፈረሰው በመስቀል ላይ በተፈጸመ የክርስቶስ ቤዛነት ነው። «በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳ በሥጋው አፈረሰ፤» እንዲል (ኤፌ. ፪፥፲፭)

ዕርቅ የተፈጸመበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል ዕርቅ የተፈጸመበት ፣ሰውና እግዚአብሔር የታረቁት በመስቀል ላይ በተፈጸመ ካሳ ነው። ሰውና እግዚአብሔር በመታረቃቸው ነፍስና ሥጋ፣ሰውና መላእ ክት፣ሕዝብና አሕዛብም ታርቀዋል። እኛ በበደልን እርሱ ክሶ (የደም ካሣ ከፍሎ) ታርቆናል።«ጠላቶቹ ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ታረቅን።» ይላልና (ሮሜ ፭፥፲፤ ፪ኛ ቆሮ. ፭፥፲፰፤ ኤፌ. ፪፥፲፮) በሌላ በኩል ደግሞ «ሁሉንም በእርሱ ይቅር ይለው ዘንድ በመስቀሉ ላይ ባፈሰሰው ደም በምድርና በሰማይ ላሉ ሰላምን አደረገ።» የሚልም አለ (ቈላ. ፩፥፳)
አምላካዊ ይቅርታ የተገኘበት ነው፤ «አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው።» በማለት ገር ፈው የሰቀሉትን በቃሉ ይቅር ብሎአቸዋልና (ሉቃ. ፳፫፥፴፬) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ፦ በሞቱ የሰውን ዘር በጠቅላላው ይቅር እንዳለው ሲናገር፦ «አሁን ግን በፊቱ ለመቆም የተመረጣችሁና ንጹሓን፥ ቅዱሳንም ያደርጋችሁ ዘንድ በሥጋው ሰውነት በሞቱ ይቅር አላችሁ።» ብሏል (ቈላ. ፩፥፳፪)

አምላካዊ ሰላም የተሰጠበት የተገኘበት ቅዱስ መስቀል

ነቢዩ ኢሳይያስ «ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም (ወልድ) ተሰጥቶናልና፥ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል።» በማለት ትንቢት የተናገረለት አምላክ ፍጹም ሰላምን የሰጠን በመስቀሉ ላይ በፈጸመው ቤዛነት ነው። (ኢሳ. ፱፥፯) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም፦ «መጥቶም ቀርበን ለነበርነው ሰላምን፥ ርቃችሁ ለነበራችሁት ለእናንተም ሰላምን ሰጠን።» ብሏል (ኤፌ. ፩፥፲፯)

የእግዚአብሔር ፍቅር የተገለጠበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል የእግዚአብሔር ፍቅር የተገለጠበት ነው። ጌታችን የማታ ተማሪ የነበረውን ኒቆዲሞስን ሲያስተምረው፦ «እግዚአብሔር አንድ ልጁን ቤዛ አድርጎ እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲህ ወዶታልና፤»ብሎታል። (ዮሐ. ፫፥፲፮) ቅዱስ ዮሐንስም በወንጌሉ የጻፈውን የጌታችን ትምህርት መሠረት አድርጎ፦ «በዚህም የእግዚአብሔር ፍቅሩ በእኛ ላይ ታወቀ፥ በእርሱ በሕይወት እንኖር ዘንድ አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና። የእግዚአብሔርም ፍቅሩ ይህ ነው፥ እርሱ ወደደን እንጂ እኛ የወደድነው አይደለንም፥ ኃጢአታችንንም ያስተሠርይልን ዘንድ ልጁን ላከው» ብሏል (፩ኛዮሐ. ፬፥፱-፲፩)

የገነት በር የተከፈተበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል የገነት በር የተከፈተበት ነው፡፡ ጌታችን ወደዚህ ዓለም የመጣው፥ ድኅነተ ምእመናንንም በመስቀል ላይ የፈጸመው ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ተዘግታ የነበረችውን ገነትን ለመክፈት ነው። ይህም ይታወቅ ዘንድ፥ በቀኙ ተሰቅሎ፥ «አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ»እያለ ሲማጸነው የነበረውን ወንበዴ፦«እውነት እልሃልሁ፥ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ» ብሎታል(ሉቃ. ፳፫፥፵፪-፵፫)

 የምንመካበት ቅዱስ መስቀል

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፦«ነገር ግን ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት (ዓለም በእኔ ዘንድ ሙት የሆነበት)፥ እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት (እኔም በዓለም ዘንድ ሙት የሆንኩበት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክሕት ከእኔ ይራቅ፤»ብሏል፡፡ (ገላ. ፮፥፲፬)
በመሆኑም ዓለምና ቅዱስ ጳውሎስ በጌታ ደም ላይ በተመሠረተች ቤተ ክርስቲያን እና በደሙ በጸናች ወንጌል ምክንያት ተለያይተዋል። አንዳቸው ለአንዳቸው ሙት ናቸው። ዓለም ሕያው የሆነችልን፥ እኛም ሕያው የሆንላት የሚመስለን የዓለም ፈቃድ ፈጻሚዎች ከቅዱስ ጳውሎስ ልንማር ይገባል። ዓለም ታልፋለች፥ እኛም ከእሷ እንለያለንና።

ከአጋንንት የምንድንበት ቅዱስ መስቀል

በክርስቶስ ቅዱስ መስቀል ከአጋንንት ጦር እንድናለን ቅዱስ ዳዊት በትንቢት፦ «ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው፥ ከቀስት ፊት (ከአጋንንት ጦር) ያመልጡ ዘንድ ወዳጆችህም እንዲድኑ።» ያለው ስለ መስቀል ነው። (መዝ. ፶፱፥፬) በመሆኑም በመስቀል ምልክት አማትበን፥ ከአጋንንት ፈተና እንድናለን። መስቀል ኃይላችን ነው መስቀልን በእጅ መጨበጥ፥ በአንገት ማንጠልጠል፥ መሳለም በዓለም ዘንድ ሞኝነት ነው ለእኛ ለክርስቲያኖች ግን ድኅነት የተረጋገጠበት ነው። ለዚህም ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት፥ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና» በማለት ያስተማረን፡፡ (፩ኛቆሮ. ፩፥፲፰)

በመሆኑም በቀራንዮ በመስቀል ላይ አንድ ጊዜ የተገለጠ ኃይለ እግዚአብሔር እስከ ዘለዓለሙ አይለየንም። በመሆኑም ለቅዱስ መስቀሉ እንሰግዳለን። ቅዱስ ዳዊት፦ «እግሮቹ በሚቆሙበት ሥፍራ እንሰግዳለን» ባለው መሠረት የጌታችን እግሮች በመስቀል ላይ፥ ያውም በቀኖት ላይ ስለቆሙ ለመስቀሉ እንሰግዳለን። መስቀሉን በደሙ ቀድሶታልና፥ ለመስቀሉ የሚገባውን ክብር እንሰጣለን። እግዚአብሔር በረድኤት በደብረ ሲና ራስ በቆመ ጊዜ፥ «ወደዚህ አትቅረብ፥ የቆምክባት ሥፍራ የተቀደሰች ናትና፥ ጫማህን ከእግርህ አውጣ፤» በማለት ሙሴን አስተምሮታል፡፡ (ዘዳ. ፫፥፭)

እንኳን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል ይቅርና የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል የቆመበትን መሬት፥ የተቀደሰ በመሆኑ፦«አንተ የቆምክበት ሥፍራ የተቀደሰ ነውና ጫማህን ከእግር አውልቅ» በማለት ኢያሱን ሲያዘው እርሱም የታዘዘውን እንዲደረግ ተረድተናል (ኢያ. ፭፥፲፭)፡፡ እንግዲህ መሬቱን፥ አፈሩን የቀደሰ አምላክ ፦ ሥጋውን የቆረሰበትን፥ ደሙን ያፈሰሰበትን፥ ነፍሱንም አሳልፎ የሰጠበትን መስቀል አልቀደሰውም ለማለት እንዴት ይቻላል? ፈጽሞ አይቻለም።ንግሥት ዕሌኒ በብዙ ድካም ከወርቅ ዙፏኗ ወርዳ ከአፈር ላይ ተቀምጣ፥ ቆፍራ አስቆፍራ መስቀሉን አውጥታለች። ዛሬ በእኛ ዘመን የተቀበረው ዳግም በመስቀሉ ያ የተገኘው ፍቅርና ሰላም ነው።

ፍቅር በጥላቻ፥ ሰላም በጦርነት፥ አንድነት በመለያየት፥ እምነት በክሕደት፥ መንፈሳዊነት በሥጋዊነት የሕዝቦች ውሕደት በዘረኝነት ቆሻሻ ተቀብሮአል። ይህንን ቆፍረን ካወጣን ያን ጊዜ የዘመኑ ዕሌኒዎች እንሆናለን። መስቀሉን ተሸክመን በጥላቻና በዘረኝነት ቆሻሻ የተቀበርንም በቅድሚያ ራሳችንን ቆፍረን እናውጣ፥ ለብዙዎችም እንቅፋት አንሁን። ዘመኑን ከተቀበርንበት የምንወጣበት ያድርግልን።

የእግዚአብሔር ቸርነት፥ የድንግል ማርያም አማላጅነት፥ የመስቀሉ በረከት አይለየን፥ አሜን።