በዓለ ደብረ ታቦር!

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐሥሩን ደቀ መዛሙርት በእግረ ደብር ትቶ ሦስቱን የምስጢር ደቀ መዛሙርት የተባሉትን ቅዱስ ጴጥሮስን፣ ቅዱስ ዮሐንስንና ቅዱስ ማርቅዱስን ይዞ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ የወጣበትና በዚያም ከመቃብር ሊቀ ነቢያት ሙሴን፣ ከብሔረ ሕያዋን ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን አምጥቶ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ዕለት በማሰብ ነሐሴ ፲፫ ቀን በየዓመቱ በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

ደብረ ታቦር ከዘጠኙ ዐበይት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓላት አንዱ ሲሆን በዓሉም በምእመናን ዘንድ ቡሄ በመባል ይታወቃል፡፡ በዓለ ደብረ ታቦር ለምን ቡሄ ተባለ? ቡሄ ማለት ‘መላጣ፣ ገላጣ’ ማለት ነው፡፡ ታቦር ተራራ ከገሊላ ባሕር በምዕራባዊ ደቡብ በኵል ዐሥር ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከናዝሬት ከተማ በስተ ምሥራቅ፣ ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተ ምዕራብ አቅጣጫ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል በርካታ ታላላቅ ተራሮች እያሉ ለምን ደብረ ታቦርን መረጠ? ብለን መጠየቃችን አይቀርም፡፡   

ምሥጢረ መንግሥቱን ለምን በታቦር ተራራ ላይ ገለጸ?

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ሌሎች ተራሮች እያሉ ደብረ ታቦር ላይ ክብሩን የገለጠው ስለ ሁለት ምክንያት ነው፡፡ እነርሱም፡- ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ ትንቢቱን ለመፈጸም ማለታችን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፣ ስምህንም ያመሰግናሉ” እያለ እንደዘመረው (መዝ. ፹፰፥፲፪) ይህን ትንቢትንም ለመፈጸም በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ክብረ መንግሥቱን ገለጠ፡፡

ሁለተኛው ደግሞ ምሳሌውን ለመፈጸም ጌታችን በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ተገለጠ፡፡ ቀድሞ ባርቅና ሠራዊቱ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ ወጥተው ሲሳራን ድል አድርገውበታልና (መሳ. ፬፥፮) ጌታም በልበ ሐዋርያት ጥርጥርን እና ፍቅረ ሢመትን (የሥልጣን ፍቅር) ያሳደረ ሰይጣንን ድል ነስቶላቸዋል፡፡ ከዚህም በመነሣት የደብረ ታቦር በዓል “የደቀ መዛሙርት (የተማሪዎች በዓል)” ተብሎም ይጠራል፡፡

እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ሥራ በመሥራታቸው በአሶር በነገሠው በከነዓን ንጉሥ በኢያቡስ እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፤ የሠራዊቱም አለቃ ሲሣራ ነበር፡፡ ዘጠኝ መቶ የብረት ሰረገሎች ነበሩትና የእስራኤልንም ልጆች ሃያ ዓመት አስጨነቃቸው፡፡ (መሳ. ፬፥፩-፫) በዚያም ወራት የለፊዶት ሚስት ነቢይቱ ዲቦራም እስራኤልን ትገዛቸው ነበር፡፡ ባርቅን ጠርታ “ሄደህ ወደ ታቦር ተራራ ውጣ፣ ከአንተም ጋር ከንፍታሌምና ከዛብሎን ልጆች ዐሥር ሽህ ሰዎች ውሰድ፤ እኔም የኢያቢንን ሠራዊት አለቃ ሲሣራን፣ ሰረገሎቹንም፣ ሕዝቡንም ሁሉ ወደ አንተ ወደ ቂሶን ወንዝ እሰበስባለሁ፤ በእጄም አሳልፌ እሰጥሃለሁ” አለችው፡፡ ዲቦራም ከደባርቅ ጋር ወደ ቃዴስ ሄደች፡፡ ሲሣራም ባርቅ ከሠራዊቱ ጋር ወደ ደብረ ተራራ እንደ ወጣ ሰማ፡፡ ባርቅ ሠራዊቱን ይዞ ከደብረ ታቦር ተራራ በወረደ ጊዜ ሲሣራና ሠራዊቱን አስደነገጣቸው፡፡ ሲሣራም ከሰረገላው ወርዶ በእግሩ ሸሸ፡፡ ባርቅም ሲሣራንና ሠራዊትን ድል ነስቶበታል፡፡ (መሳ. ፬፥፩-፲፯)

ሦስቱን ሐዋርያት ብቻ ይዞ ለምን ወደ ደበረ ታቦር ተራራ ወጣ?

፩. ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊሊጶስ ቂሳርያ ደቀ መዛሙርቱን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?” ብሎ ጠየቃቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ!” ብሎ መሰከረ፡፡ (ማቴ. ፲፮፥፲፮) ቅዱስ ጴጥሮስ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት የመሰከረውን ምስክርነት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ይሰሙ ዘንድ፣ ከነቢያት (ሙሴና ኤልያስ) አንደበት ይረዱ፣ በተዓምራት የደነደነ ልባቸውን ይከፍት ዘንድ የጌታችንን ነገረ ተዋሕዶ ከመሰከረ ከስድስት ቀን በኋላ አዕማድ ሐዋርያት ተብለው የተጠሩትን ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ያዕቆብና ቅዱስ ዮሐንስን ይዞ ወደ ተራራ አወጣቸው (ማቴ. ፲፯፥፩-፲)፡፡

፪. ሙሴን ከመቃብር፣ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን ለምን አመጣቸው?

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከሕግ (ከኦሪት)፣ ነቢዩ ኤልያስ ደግሞ ከታላላቅ ነቢያት የተመረጡበት ሌላው ምክንያት እግዚአብሔር በዘመነ ኦሪት ከሙሴ ጋር ቃል በቃል በደመና በሚነጋገርበት ጊዜ ሙሴ “ፊትህን (ክብርህን) አሳየኝ” ብሎ እግዚአብሔርን በጠየቀው ጊዜ “ሰው አይቶኝ አይድንምና ፊቴን ማየት አይቻልህም“ ብሎታል፡፡ በዚህም ብቻ ሳያበቃ “እስከ አልፍም ድረስ እጄን በላይህ እጋርዳለሁ፤ በዚያ ጊዜ ጀርባዬን ታያለህ፤ ፊቴን ግን ለአንተ አታይም” ብሎታል፡፡ (ዘፀ.፴፫፥፲፫-፳፫)

በፊልጶስ ቂሳርያ ጌታ ሐዋርያትን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደሆነ ይሉታል?” ብሎ ለጠየቃቸው ጥያቄ ሲመልሱ “ሙሴ ነው ይሉሃል ፤ እንዲሁም የኃይል ሥራህን ተመልክተው ኤልያስ ነው ይሉሃል” ብለው ነበር፤ ሙሴን ከመቃብር፤ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ “አንተ በኋለኛው ዘመን ምስክር ትሆነኛለህ” ብሎት ነበርና ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ “የኤልያስን ጌታ ኤልያስ ነው ይልሃል? እግዚአ ኤልያስ፤ አምላከ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ” ሲል በደብረ ታቦር ተገኘ፡፡ ታያለህ የተባለው ሙሴም አየ፣ ትመሰክራለህ የተባለው ኤልያስም መሰከረ፡፡

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ “ጌታ ሆይ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው” ሲል ተደምጧል፡፡ ቃል በቃል ስናየው ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታ ሆይ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ማለቱ “አንተ እያበላኸን እየፈወስከን፣ ሙሴ እነዚህ መከራ ያደርሱቡኛል ይገድሉኛል ያልካቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያን እንዳይመጡ በደመና እየጋረደ፣ ቢመጡም አልያስ እሳት እያዘነመ እያባረራቸው በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ሲሆን ምሥጢራዊው መልእክቱ ግን “የኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት በሚታመንበት፣ ወልድ ዋሕድ በምትለው ሃይማኖት መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ ሰይጣን ድል በተደረገባት በታቦር ተራራ ምሳሌም በምትሆን በወንጌል ሕይወት፣ በቤተ ክርስቲያን መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ነው፡፡

ወቅቱ በሀገራችን የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ብርሃን የሚገለጥበት፣ ወገግታ የሚታይበት፤ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚሸጋገርበት ወቅት በመሆኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት እንዲሉ፡፡ እንዲሁም በዓለ ደብረ ታቦር ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት፤ ብርሃን የታየበትና ድምፀ መለኮቱ የተሰማበት ዕለት ስለሆነ ‘የብርሃን’ ወይም ‘የቡሄ’ በዓል ይባላል፡፡

በዚህ ሰሞን ልጆች የተገመደ ገመድ አዘጋጅተው ማጮሃቸው ሁለት ዓይነት ምስጢር የያዘ ትውፊታዊ ተግባር ነው፡፡ የመጀመሪያው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ግርፋቱንና ሞቱን እናስብበታለን፡፡ ሁለተኛው ደግሞ፤ ጅራፍ ሲጮህ እንደሚያስደነግጥ ሁሉ ከጌታ ጋር የነበሩት ሦስቱ ደቀ መዛሙርትም አብ በደመና ሆኖ ሲናገር መደንገጣቸውንና መውደቃቸውን የሚያስታውስ ነው፡፡ ድምፁን ስንሰማ የባሕርይ አባቱን የአብን ምስክርነት ቃል፤ እንደ ነጎድጓድ ድምፅ ያስታውሰናል፡፡

እናቶችም ለዚህ በዓል የሚሆን ዳቦ ለመጋገር ስንዴያቸውን ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉ ይሰነብታሉ፡፡ በበዓሉ ዋዜማ (ነሐሴ ፲፪ ቀን) ሕፃናት በየቤቱ እየዞሩ ቡሄ በሉ፤ ቡሄ መጣ፤ ያ መላጣ፤ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ … እያሉ ይጫወታሉ፡፡ በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ እያነሡ ይሰጧቸዋል፡፡ ለምን ሙልሙ ዳቦ ተዘጋጅቶ ለልጆች ይሰጣቸዋል ስንል፡- ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዕለት እረኞች ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል፡፡ ‘ቡሄ’ ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና በበዓሉ ችቦ የሚበራውም ከዚህ ታሪክ በመነሣት ነው፡፡

ጌታችን በፊታቸው ተለወጠ፤ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ

ሦስቱ ሐዋርያትና ሁለቱ ነቢያቱ በተራራው ሳሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሲጸልይ ሳለ መልኩ በፊታቸው ተለወጠ፡፡ ፊቱም እንደ ፀሐይ ብሩህ ሆነ፡፡ ልብሱም እንደ በረድ ጸዓዳ ሆነ፡፡ ጌታችን “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” እንዳለ የሕይወት ብርሃን፣ የሰው ልጆች ተስፋ የሆነውን ብርሃኑን ገለጠ፡፡ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብትንም ብርሃን ያለበሰ እርሱ ነው፡፡ ለመላእክት፣ ለጻድቃን ለቅዱሳን ሁሉ የጽድቅ ብርሃንን ያደለ የማይጠፋ ብርሃን እርሱ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ተራራ ብርሃነ መለኮቱን ገለጠ፡፡ ይህ ሁሉ ነገረ ተዋሕዶን እንዲረዱ የተደረገ መገለጥ ነው፡፡ ሰውነቱን አልካዱም፣ አምላክነቱን ግን ተጠራጥረው ነበርና አምላክነቱን ገለጠላቸው፡፡  

ቅዱስ ጴጥሮስም የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፊቱ ብሩህ መሆን፣ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ መሆን እንደዚሁም የቅዱሳን የነቢያት መምጣት እና ከጌታችን ጋር መነጋገራቸውን ከሰማ በኋላ “እግዚኦ እግዚእ ሠናይ ለነ ኃልዎ ዝየ፤ ጌታ ሆይ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው“ አለ፡፡ ቅዱሳን ነቢያቱ የወትሮ ሥራቸውን እየሠሩ ማለትም ሙሴ ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላት እያስገደለ፤ ኤልያስም ሰማይ እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናመ እያቆመ፤ አንተም አምላካዊ የማዳን ሥራን እየሠራህ ገቢረ ተአምራትህን እያሳየህ፤ በዚህ በተቀደሰ ቦታ በደብረ ታቦር መኖር ለእኛ እጅግ መልካም ነው” አለ፡፡ አምላካዊ ፈቃድህስ ከሆነ በዚህ ተራራ ላይ አንድ ለአንተ፤ አንድ ለሙሴ፤ አንድ ለኤልያስ ሦስት ዳስ እንሥራ ብሎም ጠየቀ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ “በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” ሲል ጌታችን በተአምራቱ ሲራቡ እያበላቸው፣ ሲጠሙ እያጠጣቸው፣ ሲታመሙ እየፈወሳቸው፣ ቢሞቱ እያነሣቸው፤ ሙሴም እንደ ቀድሞው ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላትን እየገደለ፤ ኤልያስ ደግሞ ሰማይን እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናም እያቆመ በደብረ ታቦር ለመኖር መሻቱን ያመለክታል፡፡ ዳግመኛም “ሦስት ጎጆ እንሥራ፤ አንዱን ለአንተ፤ አንዱን ለሙሴ፤ አንዱን ለኤልያስ” በማለት የእርሱንና የሁለቱን ሐዋርያት ጎጆ ሳይጠቅስ አርቆ መናገሩ በአንድ በኩል ነቢያቱን አስቀድሞ ባልንጀሮቹ ሐዋርያትን አለመጥቀሱ ትሕትናው ትሕትናውን፤ እንደዚሁም ከጌታችን ጋር ለመኖር ያለውን ተስፋ ያመለክታል፡፡  

የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ሲናገር ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፡፡ በደመናም “ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ፤ ልመለክበት የወደድኩት ለምስጢረ ተዋሕዶ የመረጥኩት የምወደው፣ የምወልደው ልጄ ይህ ነው እርሱንም ስሙት” የሚል ቃል መጣ፡፡ በዚህም የሥላሴ ምስጢር ለዓለም ተገለጸ፡፡ እግዚአብሔር አብ በደመና ሆኖ “የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው” እያለ፣ እግዚአብሔር ወልድ ሥጋን ተዋሕዶ ፍጹም አምላክ ሲሆን ፍጹም ሰውም ሆኖ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በነጭ ደመና ተመስሎ ተገልጸዋል፡፡ ስለዚህም ደብረ ታቦር ጌታችን ብርሃነ መለኮቱ፣ ክብረ መንግሥቱ የገለጠበት እንዲሁም የሥላሴ አንድነትን ሦስትነት የተገለጠበት ነው ብላ ቤተ ክርስቲያናችን ታስተምራለች፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መምህር አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ .ም፣ ገጽ ፫፻፲፭፫፻፲፯፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ ፳፻፯ .ም፣ ገጽ ፻፲፩፡፡       

ክረምትና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ለመደበኛው ትምህርት ራሳቸውን በማዘጋጀት በውጤት ታጅበው ለሚቀጥለው ዓመት ለመሸጋገር አቅማቸውን ሁሉ ተጠቅመው ጊዜአቸውን ሰጥተው ሲተገብሩ ማየት የተለመደ ነው፡፡ “የሚተክልም የሚያጠጣም አንድ ናቸው፤ ሁሉም እንደ ድካማቸው ዋጋቸውን ይቀበላሉ” (፩ኛ ቆሮ. ፫፥፰) ተብሎ እንደተጻፈው ድካሙ ብዙ ነው፡፡ ነገር ግን በራስ ጥረት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔርም ፈቃድና ድጋፍ እንደሚያስፈልግ መረዳት ይገባል፡፡ “እኔ የወይን ግንድ ነኝ፤ ቅርንጫፎቹም እናንተ ናችሁ፤ በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ ብዙ ፍሬ የሚያፈራ እርሱ ነው፤ ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና፡፡” (ዮሐ. ፲፭፥፭) በማለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደነገረን ከእርሱ ጋር መሆን ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔርን የሚፈልግ ልብ በፍሬ ይታጀባልና፡፡

በወጣትነት ለሥጋዊው ሕይወት መውጣት መውረድ እንደለ ሆኖ ለመንፈሳዊው ሕይወትም ጊዜ መስጠት፣ በጸሎት መትጋት፣ በንስሓ መመላለስ፣ ከበጎ ነገር ጋር መተባበር ከአንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን የሚጠበቅ ጉዳይ ነው፡፡ ሥጋን ብቻ ለማስደሰት በመሮጥ መንፈሳዊ ምግብ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል ብንዘነጋ ምን እናተርፋለን? ስለዚህ ወጣቶች (የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች) ለመንፈሳዊ ሕይወታችው ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጡና በመንገዱም ሊመላለሱ ይገባል፡፡

በወጣትነት ዘመን ስሜታዊነት የሚንጸባረቅበት ጊዜ ነው፡፡ ይህን ጊዜ በጥበብና በማስተዋል ማለፍ ካልተቻለ ለተለያዩ ክፉ ሥራዎች (ሱሶች፣ እግዚአብሔርን መርሳት፣ በጎ ነገርን አለማድረግ፣ …) መጋለጥን ያስከትላል፡፡ በተለይም እግዚአብሔርን አለማሰብ እንደ ቃሉም አለመመላስ በቀሪው ሕይወታቸው የሚያሳድረው ተጽእኖ ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን ዐስብ” (መክ. ፲፪፥፩) አንዲል በወጣትነት ፈጣሪን መፈለግ ይገባል፡፡ ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን ከሕፃንነት ጀምሮ በሰንበት ት/ቤት እንዲታቀፉ፣ የእግዚአብሔርንም ቃል እየተማሩ እንዲያድጉ የምታደርገው፡፡  

ማኅበረ ቅዱሳንም አገልግሎቱን በግቢ ጉባኤት ላይ በማተኮር ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ላይ በመሥራት የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል፡፡ ለተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው በተጓዳኝ መንፈሳዊ ትምህርትን በማስተማር፣ ሕይወታቸውን እንዲፈትሹ፣ ውጤታማም ሆነው እንዲወጡና በኦርቶዶክሳዊ እምነታቸው እንዲጸኑ ከፍተኛ ጥረት ያደርጋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችም የቀሰሙትን መንፈሳዊ ዕውቀትና ሕይወት ወደ ተግባር ለመለወጥ የሚረዳቸው ጊዜ ቢኖር በክረምቱ ወራት ትምህርት ተዘግቶ ወደ ቤተሰቦቻቸው ለዕረፍት ሲሄዱ ነው፡፡ በዚህ ወቅት የዕረፍት ጊዜያቸውን በአግባቡ ሊጠቀሙበት ይገባል፡፡ ዕረፍት ላይ መሆናቸው ሊያዘናጋቸው ስለሚችል አገልግሎቱ ላይ በማተኮር ራሳቸውን እንዲጠብቁ በአጥቢያቸው በሚገኝ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ በመሳተፍ እንደተሰጣቸውም ጸጋ ማገልገል፣ ዕውቀታቸውን ማካፈል፣ ለሌችም አርአያ መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡  

ሌላው በክረምት ወቅት የግቢ ጉባኤት ተማሪዎች ሊያደርጉት የሚገባው በተለያዩ በጎ አድራጎት ሥራዎች ላይ በመሳተፍ በተሰጣቸው ዕውቀት፣ ገንዘብና ጉልበት የተቸገሩትን በመደገፍ ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ዕረፍት ላይ መሆናቸው በርካታ በጎ ሥራዎችን ለመሥራት ዕድሉን ይፈጥርላቸዋል፡፡ “ለሥራ ከመትጋት አትስነፉ፤ በመንፈስ ሕያዋን ሁኑ፤ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ ለጸሎት ትጉ፡፡ በችግራቸው ቅዱሳንን ለመርዳት ተባበሩ፤ እንግዳ መቀበልንም አዘውትሩ” (ሮሜ. ፲፪፥፲፩-፲፬) በማለት እንደተነገረና ክረምቱ ምቹ ጊዜ በመሆኑ መትጋት ይገባል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሌላው በክረምት ወቅት ሊያደረጉት የሚገባቸው ነገር ቢኖር ለአብነት ትምህርት ትኩረት ሰጥተው ይማሩ ዘንድ ነው፡፡ አንዳንድ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የመደበኛ ትምህርቴን በደንብ እንዳልከታተል እንቅፋት ይሆንብኛል እያሉ በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠውን የአብነት ትምህርት ከመማር ችላ የሚሉ አሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ግን  ጊዜን መድቦ በዕቅድ ራስን ካለመምራት ጋር የሚመነጭ በመሆኑ ሲሸሹ ይታያሉ፡፡  ነገር ግን አጠገባቸው ያሉት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ጊዜአቸውን በአግባቡ በመጠቀም የአብነት ትምህርትን በመማር ለክህነት ሲበቁ እንመለከታለን፡፡ ስለዚህ በመንፈሳዊው ሕይወት ራስን ለማሳደግና በጎደለው ቦታ በመሙላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል በአጥቢያቸው በሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ወይም አቅራቢያቸው ባለ አብነት ትምህርት ቤት ገብተው መንፈሳዊውን ትምህርት መማር ይጠበቅባቸዋል፡፡

የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በክረምቱ ሰፊ ጊዜ ስለሚኖራቸው ሳይዘናጉ ከሌሎች በጎ አድራጎት ሥራዎችና አገልግሎት በተጓዳኝ ለሚቀጥለው ዓመት ትምህርታቸው የሚያግዟቸውን መጻሕፍት በመመርመር ለአዲሱ ዓመት ትምህርት ራሳቸውን ማዘጋጀትም ይገባቸዋል፤ ካለ ንባብ የሚያሳልፉት ቀን ሊኖር አይገባምና፡፡

በአጠቃላይ በክረምት የዕረፍት ወቅት እንደመሆኑ በመዝናናትና በስንፍና በመመላለስ የገነቡትን መንፈሳዊ ሕይወት ችላ እንዳይሉ ጥንቃቄ በማድረግ ባላቸው ጊዜ ራሳቸውንና ሌሎችን በመርዳት ከበረከቱ እንዲሳተፉ ያስፈልጋል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ፅንሰታ ለማርያም

ቅደስት ቤተ ክርስቲያናችን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችበትን ዕለት ነሐሴ ፯ ቀን በየዓመቱ በድምቀት ታከብረዋለች፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላጆች በእናቷ ሐና በኩል ቅድመ አያቶቿ ጴጥሪቃና ቴክታ ደጋጐችና እግዚአብሔርን የሚፈሩና በፍጹም ልቡናቸው እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ነበሩ፡፡

እግዚአብሔርን ማምለክ ብቻ ሳይሆን በባለጠግነታቸውም የታወቁ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ልጅ ስላልነበራቸው በጣም ያዝኑና ይተክዙ ስለነበር አንድ ቀን ጰጥሪቃ የሀብቱን ብዛት ተመልክቶ ሚስቱን (ቴክታ)ን “ያለን ገንዘብና ንብረት እንኳን ለእኛ ለልጅ ልጆቻችን የሚተርፍ ነው፡፡ ነገር ግን ወራሽ ልጆች የሉንም” እያለ በትካዜ ተናገራት፡፡ ቴክታም ከእርሷ ልጅ ባለመውለዱ ሌላ ወላድ ሴት የፈለገ መስሏት ‘እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ነውና ሌላ አግብተህ ወለድ” አለቸው በትካዜ ውስጥ ሆና፡፡  

ጴጥሪቃም “ይህንንስ በልቤ እንዳላሰብኩና እንዳልተመኘሁ እግዚአብሔር ያውቃል” በማለት ተናገራት፡፡ ቴክታም በሐዘን ወስጥ ሆና ሳለች ራእይ ታያለች፤ ነጭ እንቦሳ ከማሕኅፀኗ ስትወጣ፤ እንቦሳዪቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ሰባት ስትደርስ፣ ሰባተኛዋ ጨረቃን ስትወልድ፤ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ አየች። እርሷም ባየችው ራእይ ተገርማ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ አደነቀች፡፡ “በሕልሜ ነጭ ጥጃ ከማኅፀኔ ስትወጣ፣ ያችም ነጭ ጥጃ ደግሞ ነጭ ጥጃ ስትወልድ፣ እንደዚህ እየሆነ እስከ ሰባት ትውልድ ሲደርሱ ሰባተኛዪቷም ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋ ደግሞ ፀሐይን ስትወልድ አየሁ” በማለት አስረዳችው።

ጰጥሪቃም ባለቤቱ ባየችው ራእይ ተደንቆ ሕልም ለሚፈታ ሰው የሚስቱን ራእይ ተናገረ፡፡ ሕልም ተርጓሚውም ምስጢር ተገልጾለት “ሰባት አንስት ጥጆች መውለዳችሁ ሰባት ሴቶች ልጆች ይወለዳሉ፤ ነጭ መሆናቸው ደጋጎች ልጆች መሆናቸውን ሲያመለክት፤ ሰባተኛዪቱ ጨረቃን መውለዷ ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ናት፤ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም” በማለት ተረጐመለት፡፡ ጰጥሪቃም በተተረጎመለት ራእይ ተገርሞ ለሚስቱ ነገራት፤ እርሷም “የእስራኤል አምላክ የሚያደርገውን እርሱ ያውቃል” በማለት ፈጣሪዋን አመሰገነች፡፡

ቴክታ ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ሔሜን አሏት፤ ሔሜን – ዴርዴን ወለደች፤ ዴርዴም – ቶናን፤ ቶናም – ሲካርን ወለደች፤ ሲካርም – ሴትናን፤ ሴትናም – ሔርሜላን ወለደች፤ ሔርሜላም የተከበረችና የተመረጠች ዓለሙን ሁሉ ለፈጠረ ጌታ አያት ለመሆን የበቃችውን ሐናን ወልዳለች። ሐና በመልካም አስተዳደግ አድጋ አካለ መጠን ስታደርስ ከነገደ ይሁዳ ከመንግሥት ወገን የተወለደ የቅስራ ልጅ የአልዓዛር የልጅ ልጅ ከሚሆን ከኢያቄም ጋራ አጋቧት፡፡ ሁለቱም ወደ ቤተ እግዚአብሔር ዕለት ዕለት በመሄድ ለዐይናቸው ማረፊያ ለልባቸው ተስፋ የሚሆን ልጅ እንዲሰጣቸው ይለምኑ ነበር፡፡

ከዕለታት በአንደኛው ቀን ሁለቱም ወደ ቤተ እግዚአብሔር ሄደው ሲጸልዩ ውለው ሲመለሱ ርግቦች ከልጆቻቸው ጋር ደስ ብሏቸው ሲጫወቱ አይተው ሐና “አቤቱ ጌታዬ ግዕዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሣኸኝ?” ብላ ምርር ብላ አለቀሰች፡፡ ወዲያው ሳይውሉ ሳያድሩ ሱባኤ ይገባሉ፤ ኢያቄም ወደ በረሃ ሄዶ ሲጸልይ ሐና ደግሞ በቤቷ ዙሪያ ባለው የአትክልት ቦታ ሱባኤ ያዘች፤ በሱባኤያቸው ፍጻሜም ሁለቱም ራእይ አይተው ተነጋግረዋል፡፡

ኢያቄም “ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ብሎ የተገለጸለትን ለሐና ነግሯታል፤ ይኸውም የራእዩ ምስጢር፡- ወፍ የተባለው አካላዊ ቃል ክርስቶስ ሲሆን፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባሕርዩ ነው፤ ከላይ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ማለቱ የኢያቄምን ባሕርይ ባሕርይ እንደሚያደርግ ሲያጠይቅ ሲሆን፤ ሰባቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ምልአቱ፣ ስፍሐቱ፣ ርቀቱ፣ ልዕልናው፣ ዕበዩ ናቸው፡፡

ሐናም ተገልጾላት ለባሏ “ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ” አለችው። ምስጢሩም፡- ርግብ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትሆን፤ ነጭነቷ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ዘላለማዊ ድንግልናዋ ነው፤ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ ወደ ዦሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በዦሮዋ ሰምታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን የምትፀንሰውን ንጽሕት ርግብ የተባለችውን እመቤታችንን የምትወልድ መሆኗን ሲያጠይቅ ነው፡፡

ኢያቄምና ሐናም ይህንን ራእይ ሐምሌ ፴ ቀን ካዩ በኋላ “ወንድ ልጅ ብንወልድ ወጥቶ ወርዶ ይርዳን አንልም ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ይሆናል፤ ሴትም ብንወልድ ለቤተ እግዚአብሔር መጋረጃ ፈትላ ትኑር” ብለው ስእለት ከተሳሉ በኋላ ራእይ አየን ብለው ዕለቱን አልተገናኙም፤ አዳምንና ሔዋንን “ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሏት” ብሎ የተናገረው አምላክ ለእኛም ይግለጽልን ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ ሰባት ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ።

ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን “ከሰው የበለጠች ከመላእክት ሁሉ የከበረች ልጅ ትወልዳላችሁ” ብሎ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለሐና ነግሯት በፈቃደ እግዚአብሔር በብሥራተ መልአክ እመቤታችን ነሐሴ ሰባት ቀን እሑድ ተፀንሳለች፡፡ ለዓለም ሁሉ የድኅነት መገኛ የሆነች ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችበት ዕለት ነሐሴ ሰባት የተባረከች እንደመሆኗ መላው ክርስቲያን በዓሏን ሊያከብር ይገባል፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በከበሩ ኢያቄምና ሐና ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸው ከእኛ ጋር ይኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ከመጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ነሐሴ

       መጋቤ ሐዲስ ዶ/ር ሮዳስ ታደሰ፣ ነገረ ማርያም በሐዲስ ኪዳን

የጾመፍልሰታየዕለታትምንባባት፣ ምስባክ፣ ወንጌልና ቅዳሴ

ነሐሴ ፩

ምንባባት

. ፩ኛጢሞ. ፭ ፥፲፩

. ፩ኛዮሐ. ፭፥ ፩-፮

. ግብ.ሐዋ. ፭ ፥፳፯-፴፬

ምስባክ

. ወእነግር ስምዐከ በቅድመ ነገሥት ወኢትይኀፈር፤

ወአነብብ ትእዛዘከ ዘአፍቀርኩ ጥቀ፤

ወአነሥእ እደውየ ኀበ ትእዛዝከ ዘአፈቅር

ወንጌል

. ዮሐ. ፲፱፥፴፰-ፍጻሜ

ቅዳሴ 

. ዘዮሐንስ አፈወርቅ አው ዘእግዝእትነ

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛጢሞ. ፪፥፰-ፍጻሜ 

. ፩ኛጴጥ. ፫፥፩-፮

. ግብ.ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

ምስባክ

. ወይወስዱ ለንጉሥ ደናግለ ድኅሬሃ፤

ወቢጻሂ ይወስዱ ለከ፤

ወይወስድዎን በትፍሥሕት ወበሐሤት፤

ወንጌል 

. ዮሐ. ፰፥፱-፲፪

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛተሰ. ፩፥፩-ፍጻሜ

. ፩ኛ ጴጥ. ፫፥ ፲-፲፭

. ግብ. ሐዋ. ፲፬፥፳-ፍጻሜ

ምስባክ

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤

ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤

ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፤

ወንጌል 

. ሉቃ. ፲፰፥፱-፲፰

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ሮሜ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ

. ፩ ጴጥ. ፭፥፲፪

. ሐዋ. ፲፯፥፳፫-፳፰

ምስባክ

. እግዚኦ በኃይልከ ይትፌሣሕ ንጉሥ፤

ወብዙኃ ይትሐሠይ በአድኅኖትከ፤

ፍትወተ ነፍሱ ወሀብኮ፡፡

ወንጌል 

. ሉቃ. ፲፬፥፴፩-ፍጻሜ

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘቄርሎስ

ነሐሴ

ንባባት

. ፪ኛቆሮ. ፲፪፥፲-፲፯

. ፩ኛዮሐ. ፭፥፲፬-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፲፭፥፩-፲፫

ምስባክ

. ወትሰይመኒ ውስተ ርእሰ ሕዝብ፤

ሕዝብ ዘኢየአምር ተቀንየ ሊተ፤

ውስተ ምስማዐ ዕዝን ተሠጥዉኒ፤

ወንጌል

. ሉቃ. ፲፭፥፩-፲፩

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፫፥፲-፳፪

. ፩ኟ ጴጥ. ፫-፯

. ግብ.ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

ምስባክ

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤

ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤

ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፡፡

ወንጌል

. ማር. ፲፮፥፱-፲፱

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ

ምንባባት

. ዕብ. ፩፥፩-፲፯

. ፩ኛጴጥ. ፪፥፯-፲፰

. ግብ.ሐዋ. ፲፥፩-፴

ምስባክ

. ብፁዕ ብእሲ ዘአንተ ገሠጽኮ እግዚኦ፤

ወዘመሀርኮ ሕገከ፤

ከመ ይትገኀሥ እመዋዕለ እኩያት፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፲፮፥፲፫-፳፬

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

ሮሜ. ፱፥፳፬- ፍጻሜ

፩ኛጴጥ. ፬፥፲፪-ፍጻሜ  

ግብ. ሐዋ. ፲፮፥፴፭-ፍጻሜ

ምስባክ

. ወድቀት እሳት ወኢርኢክዋ ለፀሐይ፤

ዘእንበለ ይትዐወቅ ሦክክሙ ሕለተ ኮነ፤

ከመ ሕያዋን በመዓቱ ይውኅጠክሙ፡፡

ወንጌል

. ማቴ. ፯፥፲፪-፳፮

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፊልጵ. ፩፥፲፪-፳፬

. ፪ኛዮሐ. ፩፥፮-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፲፭፥፲፱-፳፭

ምስባክ

. ወትቀውም ንግሥት በየማንከ፤

በአልባሰ ወርቅ ዑፅፍት ወሑብርት፤

ስምዒ ወለትየ ወአጽምኢ እዝነኪ፡፡

ወንጌል 

. ዮሐ. ፲፥፩-፳፪

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘባስልዮስ

ነሐሴ ፲
ምንባባት

. ዕብ. ፲፪፥፳፪- ፍጻሜው 

. ፩ኛጴጥ. ፩፥፮-፲፫ 

. ግብ.ሐዋ. ፬፥፴፩-፳፭ 

ምስባክ

. ተዘከር ማኅበረከ በትረ ርስትከ፤

ወአድኀንከ በትረ ርስትከ፤
ደብረ ጽዮን ዘኀደርከ ውስቴታ፡፡

ወንጌል

. ሉቃ. ፲፮፥፱-፲፱ 

ቅዳሴ 

ዘእግዝእትነ ማርያም 

ነሐሴ ፲፩
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፭፥፲፩-ፍጻሜ  

. ፩ኛዮሐ. ፪ ቊ. ፲፬-፳ 

. ግብ. ሐዋ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜው 

ምስባክ

. ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ፤

ወትሠይሚዮሙ መላእክተ ለኵሉ ምድር፤
ወይዘክሩ ስመኪ በኵሉ ትውልደ ትውልድ፡፡

ወንጌል

.ሉቃ. ፮፥፳-፳፬ 

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ ፲፪
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፱፥፲፯-ፍጻሜ

. ይሁዳ. ቊ. ፰-፲፬ 

. ግብ.ሐዋ. ፳፬፥፩-፳፪ 

ምስባክ

. እግዚኦ ኩነኔከ ሀቦ ለንጉሥ፤

ወጽድቀከኒ ለወልደ ንጉሥ፤
ከመ ይኰንኖሙ ለሕዝብከ በጽድቅ፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፳፪፥፩-፲፭ 

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ

ነሐሴ ፲፫
ምንባባት

. ዕብ. ፲፩፥፳፫-፴ 

. ፪ኛጴጥ. ፩፥፲፭ 

. ግብ.ሐዋ. ፯፥፵፬-ፍጻሜ

ምስባክ

. ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ፤

ወይሴብሑ ለስምከ፤
መዝራዕትከ ምስለ ኃይል፡፡

ወንጌል 

. ሉቃ. ፱፥፳፰-፴፰ 

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዲዮስቆሮስ፡፡

ነሐሴ ፲፬
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፩፥፲-፲፪ 

. ያዕ. ፩፥፲፪ 

. ግብ.ሐዋ. ፲፥፴-፵፬ 

ምስባክ

. ዘአዘዝከ መድኃኒቶ ለያዕቆብ፤

ብከ ንወግዖሙ ለኵሎሙ ፀርነ፤
ወበስምከ ናኃሥሮሙ ለእለ ቆሞ ላዕሌነ፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፲፯፥፲፬-፳፬ 

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ

ነሐሴ ፲፭

ምንባባት        

. ፩ኛቆሮ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ   

. ይሁዳ. ፩፥፲፯-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፩፥፲፪-፲፭

ምስባክ   

. ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ፤

ቅዳሴ፡      

. ዘሐዋርያት

ነሐሴ ፲፮

ምንባባት       

. ሮሜ. ፰፥፴፩-ፍጻሜ   

. ዮሐ. ፪፥፩—፯  

. ግብ.ሐዋ. ፩፥፲፪-፲፭

ምስባክ፡   

. ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል፤

እግዚአብሔር ውስተ ማዕከላ ኢትትሐወክ፤

ወይረድኣ እግዚአብሔር ፍጽመ፡፡

ወዓዲ ወተዚያነዉ ዳኅናሃ ለኢየሩሳሌም፤

ወፍሥሐሆሙ ለእለ ያፈቅሩ ስመከ፤

ይኩን ሰላም በኃይልከ፡፡

ወንጌል

. ማቴ. ፳፮፥፳፮-፴፩

ቅዳሴ      

. ዘእግዚእነ

ጾመ ፍልሰታ ለማርያም

እንኳን ለፍልሰታ ለማርያም ጾም በሰላም አደረሳችሁ!

ጾመ ፍልሰታ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከደነገገቻቸው ሰባቱ የዐዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡ ይህንንም ጾም ከነሐሴ ፩-፲፮ ቀን ድረስ ለሁለት ሱባኤ ከሰባት ዓመት ሕፃናት ጀምሮ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ የሚጾሙትና በናፍቆት የሚጠበቅ ጾም ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያትን አብነት አድርጋ የምትጾመው ጾም እንደመሆኑ ምእመናን በየገዳማቱና አድባራት በመገኘት ራሳቸውን ለእግዚአብሔር በማስገዛት በሱባኤ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደትና በምሕላ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ያገኙ ዘንድ በፍጹም ፍቅርና ትጋት ይጾሙታል፡፡  

ፍልሰታ የሚለው ቃል “ፈለሰ” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም “መለየት፣ ማረግ፣ ወደ ላይ መውጣት፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መሄድ” ማለት ነው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በ፷፬ ዓመቷ ከዚህ ዓለም ድካም ጥር ፳፩ ቀን ፵፱ ዓ.ም በማረፏ  ሐዋርያት ሥጋዋን በጌቴሴማኒ ለማሳረፍ ሲወስዷት አይሁድ “እንደ ልጇ ተነሣች፤ ዐረገች እያሉ እንዳያውኩን በእሳት እናቃጥላት” ብለው በዓመፃ ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም በክፋት ተነሣስቶ አጎበሩን ይዞ ሊያወርዳት ሲል የእግዚአብሔር መልአክ ሁለት እጆቹን ቆረጠው፡፡ እግዚአብሔርም ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ እመቤታችንን በደመና ነጥቆ  ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡ ዮሐንስም በዕፀ ሕይወት ላሉት ነፍሳት “ዛቲ ይእቲ ሕይወትክሙ ኪያሃ ሰብሑ፤” ብሎ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ተቀብለው “ብፅዒት ከርስ እንተፆረትኪ ወብፅዓት ዓይንት እለእርያ ኪያኪ ፤ ሕይወታችሁ ይህቺ ናት፤ እርሷን አመስግኑ፣ አንቺን የተሸከመች ማኅፀን የተባረከች ናት፤ አንቺን ያዩ ዓይኖችም የተባረኩ ናቸው ፤” ብለው አመስግነዋታል፡፡ “ትውልድ ዘኢይሀልፍ ያመሰግኑኛል” ማለት ይህ ነው፡፡  

ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ሐዋርያቱ በተመለሰ ጊዜ ሐዋርያቱ “እመቤታችንስ?” እያሉ በጥያቄ አፋጠጡት፡፡ እርሱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገነት በዕፀ ሕይወት እንዳስቀመጣት ነገራቸው፡፡ እነርሱም ዮሐንስ ያየውን እኛም ማየት አለብን ብለው ከነሐሴ ፩-፲፬ ሱባኤ ገቡ፡፡ ጌታችንም የሐዋርያቱን ጽናት ፍቅር ተመልክቶ የእመቤታችንን ትኩስ ሥጋ ከዕፀ ሕይወት አምጥቶ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ተቀብለው በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡ በሦስተኛውም ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ ሕንድ በደመና ተጭኖ ሲመጣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በመላእክቱ ታጅባ ስታርግ ተገናኙ፡፡ ሐዋርያው ቶማስም ሐዋርያት ያዩትን እኔ ሳላይ ብሎ አዘነ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?” በማለት ከደመናው ወደ መሬት ራሱን ሊጥል ሲቃጣው እመቤታችን ማረጓን እርሱ ብቻ እንደተመለከተ ነግራ የተገነዘችበትን ሰበን ሰጥታው ዐረገች፡፡  

ሐዋርያው ቶማስ ወደ ሐዋርያት በተመለሰ ጊዜም “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው፡፡ እነርሱም “አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆናል?” አላቸው፡፡ ከሐዋርያት መካከል ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ በፊት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ ተጠራጥሮ እንደነበር በመግለጽ ገሰጸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ተቈጥቶ የእመቤታችንን ክቡር ሥጋ ለቅዱስ ቶማስ ለማሳየት ሔዶ መቃብሯን ቢከፍት የእመቤታችንን ሥጋ ሊያገኘው አልቻለም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ቆመ፡፡

ቅዱስ ቶማስም “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ስታርግ አግኝቻታለሁ” ብሎ የሰጠችውን ሰበን ለሐዋርያት ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት እየተደሰቱ ሰበኑን ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን በቅዳሴ ጊዜ ሠራዒ ዲያቆኑ በሚይዘው መስቀል ላይ የሚታሠረው መቀነት መሰል ልብስ፤ እንደዚሁም አባቶች ካህናት በመስቀላቸው ላይ የሚያደርጉት ቀጭን ልብስና በራሳቸው የሚጠመጥሙት ነጭ ሻሽ የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡

ሐዋርያትም ቶማስ ያየውን እውነት ለማየትና ከእመቤታችን በረከት ለማግኘት ከነሐሴ ፩-፲፮ በጾምና በጸሎት ተወስነው ቆይተዋል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታቸውን ሰምቶ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችንን መንበር፤ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፤ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ እመቤታችንንም ሐዋርያትንም አቍርቧቸዋል፡፡ እነርሱም እመቤታችንን በዓይናቸው ከማየት ባሻገር አብረው ሥጋውን ደሙን ተቀብለዋል /ትርጓሜ ውዳሴ ማርያም/፡፡ እንደ ልጇ እንደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ትንሣኤ” ያሰኘውም ይህ ታሪክ ነው፡፡

በጾመ ፍልሰታ በቤተ ክርስቲያናችን በየቀኑ በማኅሌቱ፣ በሰዓታቱና በቅዳሴው በሚደርሰው ቃለ እግዚአብሔር ነገረ ማርያም ማለትም የእመቤታችን ከመፀነሷ ጀምሮ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለው ታሪኳ፣ ለአምላክ ማደሪያነት መመረጧ፣ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ክብሯ፣ ርኅርራኄዋ፣ ደግነቷ፣ አማላጅነቷ፣ ሰውን ወዳድነቷ በስፋት ይነገራል፡፡ እመቤታችንን ከሚያወድሱ ድርሳናት መካከልም በተለይ ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከነገረ ማርያም ጋር በማዛመድ የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም፤ እንደዚሁም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌ (ከነገረ ክርስቶስ) እና ከነገረ ማርያም ጋር በማመሣጠር የሚያትተው ውዳሴ ማርያምም በስፋት ይጸለያል፤ ይቀደሳል፤ ይተረጐማል፡፡ በሰንበታት የሚዘመሩ መዝሙራት፤ በየዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለተዋሕዶ በእግዚአብሔር መመረጧን፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን፣ ክብሯን፣ ቅድስናዋን፣ ንጽሕናዋን የሚያወሱ ናቸው፡፡

ምእመናንም በረከት ያገኙ ዘንድ የዲያብሎስንም ፈተና ድል ይነሡ ዘንድ ከነሐሴ ፩-፲፮ ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው በየገዳማቱና በየአብያተ ክርስቲያናቱ በዓት አዘጋጅተው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው አስገዝተው ይጾማሉ፤ ይጸልያሉ፤ እንደዚሁም ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ይህ ጾም ለእመቤታችን ያለንን ፍቅር የምንገልጽበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ኦርቶዶክሳውያን ሕፃናት ከሌላው ጊዜያት በተለየ ሁኔታ ትምህርተ ወንጌል የሚማሩት፤ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሚቀበሉት በዚህ በጾመ ፍልሰታ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋና በረከት አይለየን፡፡

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፤

በሀገራችን በኢትዮጵያና በመላው ዓለም የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፡-

የክብር ባለቤት እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሰባት ዓ.ም የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ!

‹‹ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፤ ነፍሴ እግዚአብሔርን እጅግ ታከብረዋለች›› (ሉቃ. ÷፵፮)

ይህንን ዐረፍተ ነገር የተናገረችው ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በሠራው ስሥራ ሰውነታችንን ለመዋሐድ የመረጣት ምርጥ የፍጥረት ወገን ናት፤ ፍጥረት ሁሉ በእግዚአብሔር ለእግዚአብሔር ተፈጥሮአል፤ የእግዚአብሔርም ነው፤ የቅድስት ድንግል ማርያም መመረጥም በእግዚአብሔር ለሰው የተደረገ ምርጫ ነው፤

የሰው መዳን ከጥንቱ ከጠዋቱ በእግዚአብሔር ልዩ አሠራር እንደሚከናወን በነቢያት የተገለጸ ነበረ፣ ‹‹አኮ በተንባል ወአኮ በመልአክ አላ ለሊሁ እግዚእ ይመጽእ ወያድኅነነ፤ በአማላጅም አይደለም፤ በመልአክም አይደለም እሱ ራሱ ጌታ መጥቶ ያድነናል እንጂ›› የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ትንቢትም ይህንን ያስረዳል፤ ቃለ ትንቢቱ ድኅነታችን በጌታ ቤዛነት እንደሚከናወን ያረጋግጣል፤ ይህም ሊሆን የቻለው ከፍጡራን ወገን በደሙ ቤዛነት ፍጡራንን የሚያድን ስለሌለ ነው፤

ከዚህ አንጻር የሰው መዳን በእግዚአብሔር አሠራር በደም ቤዛነት ከሆነ፣ በደሙ ቤዛነትም ዓለምን ማዳን የሚችል ከፍጡር ወገን ከሌለ፣ መዳናችን በእግዚአብሔርና በእግዚአብሔር እጅ ብቻ የተንጠለጠለ ነበረ፤ እግዚአብሔር በደሙ ቤዛ ሆኖ ዓለምን ለማዳን ደግሞ ደም ሊኖረው ይገባ ነበር፤ በመሆኑም እግዚአብሔር በክዋኔው ደም የሌለው ስለሆነ ለቤዛ ዓለም የሚፈስ ደምን ገንዘብ ማድረግ ነበረበት፤ ይህንን ደም ለመዋሐድ ቅድስት ድንግል ማርያምን መረጠ፤ ለዚህ ብቁ እንድትሆንም በእስዋ ላይ ሥራውን ሥራ፤ በምርጫውም መሠረት ከቅድስት ድንግል ማርያም ደማዊ ሥጋንና ነፍስን ተዋሕዶ ለቤዛዊ መሥዋዕት መንገዱን አመቻቸ፤

ቅድስት ድንግል ማርያም በነገረ ድኅነት መሰላል ለመሆን በእግዚአብሔር የተመረጠች በመሆኗ አንቀጸ አድኅኖ ወይም የድኅነት በር ትባላለች፤ ቅድስት ድንግል ማርያም ለዚህ ታላቅ ነገረ ድኅነት መመረጥዋ እጅግ ታላቅ ዕድል መሆኑን ስለተገነዘበች ‹‹ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና›› በማለት እግዚአብሔርን በመዝሙር አመስግናለች አክብራለችም፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

የቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና እና የአምልኮ መዝሙር የኛም መዝሙር ነው፤ እግዚአብሔር ለቅድስት ድንግል ማርያም ታላላቅ ሥራዎችን እንደሠራ ለኛም ብዙ ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልናል፤ እየሠራልንም ነው፤ ለሠራልን አምላክም እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም ታላቅ ክብርን መስጠት ይገባናል፤ ለእግዚአብሔር የምንሰጠው ክብርም በቃል ብቻ የሚገለጽ ሳይሆን በተግባር የሚታይ ሊሆን ይገባል፤ የድንግል ማርያም መንፈሳዊ ሕይወት በማስተዋል በትሕትና፣ በትዕግሥት በርኅራኄ በመታዘዝ በንጽሕና በቅድስና በክብርና በበረከት የተሞላ እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ከተጻፈው ሥነ ሕይወቷ መረዳት እንችላለን፤ ታድያ በእርሷ ክብርና ተማሕፅኖ የምንተማመን ልጆቿም የእሷን ያህል እንኳ ባንችል ወደ እርስዋ የሚጠጋጋ መንፈሳዊ ሕይወት ሊኖረን ይገባል፤ ይህም የምናደርገው ለእግዚአብሔር ክብርና ለእኛ መዳን ሲባል ነው፤ እኛ እግዚአብሔርን ስናከብር እንከብራለን እንድንማለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር የማንሰጥ ከሆነ ግን ውጤቱ መክበር ሳይሆን ሌላ ነው የሚሆነው፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

እኛ በየጊዜው ጾምን እንድንጾም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት ፈቃደ ሥጋችንን በመግራት ለእግዚአብሔር ታዛዦች እንድንሆን ነው፤ ጾም የኃጢኣት መግቻ መሣሪያ በመሆኑ ‹‹ልጓመ ኃጢኣት›› ተብሎ ይታወቃል፤ በዚህም ሰውነታችንን ለግብረ ኃጢአት ከሚያጋግሉ ምግቦች አርቀን በሰከነ መንፈስ እግዚአብሔርን እያሰብን ኃጢአታችንንም እያስታወስን በንስሓ ወደ እርሱ ለመቅረብና ለሱ ለመታዘዝ እንጾማለን፤

የጾም ጥቅም ከጥንት ጀምሮ የታወቀ በእግዚአብሔርና በሰውም ተቀባይነት ያለው ነው፤ እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ መታዘዝን ይወዳልና በጾምና በጸሎት ለሱ ልንታዘዝ ይገባል፤ እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ሊያድር የቻለው ‹‹እንዳልኸኝ ይሁንልኝ›› ብላ ታዛዥነትዋን በገለጸች ጊዜ ነው፤ እኛም እንዳልከን ይሁንልን እያልን እንደ እስዋ ታዛዥ መሆን አለብን፤

ዛሬ በዓለማችን ያለው መተረማመስ ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝ ያመጣው ጣጣ እንደሆነ ማንም አይስተውም፤ መታዘዙ ቢኖር ኖሮ የሰው ልጅ ሰውን የሚያድን ብቻ እንጂ ሰውን የሚገድል መሣሪያ አያመርትም ነበር፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ወንድምህን እንደ ራስህ አድርገህ ውደድ አለ እንጂ ግደል ብሎ አላዘዘምና ነው፤ አሁንም በዚህ ባለንበት ዓለም በጣም ተባብሶ የሚገኘው የመጠፋፋት ዝንባሌ ለእግዚአብሔር በመታዘዝ በሰላምና በሰጥቶ መቀበል ካልተቋጨ ዳፋው አስከፊ መሆኑ አይቀርም፤

ከዚህ አንጻር ዛሬም ለሰው ልጆች ሁሉ የምናስተላልፈው መልእክት ‹‹በፍቅር ከሆነ ትንሹም ለሁሉ ይበቃልና ያለውን በጋራ በመጠቀም በፍቅርና በሰላም እንኑር›› የሚል ነው፤ ‹‹ፍትሕና ርትዕም ለሰው ልጅ መነፈግ የበለትም፤ ሰው በምድር ላይ ሠርቶ የመኖር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፤ ይህንን ማድረግ ማለት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ማለት ነው፤ ስለሆነም ለእግዚአብሔር ክብርና ለራሳችን መዳን ስንል ለእርሱ በመታዘዝ በሕይወትና በሰላም እንኑር፡፡

በመጨረሻም፡

በጾመ ማርያም ሱባኤ ስለ ሀገር ሰላምና ስለ ሕዝብ ደኅንነት በመጸለይ፣ በልዩ ልዩ ምክንያት በመከራ ላይ ወድቀው የሚገኙ ወገኖቻችንን በሚያስፈልጋቸው ሁሉ በመርዳት ሱባኤውን እንድናሳልፍ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን እናስተላልፋለን፤

መልካም የሱባኤ ወቅት ያድርግልን፤ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

ነሐሴ 1 ቀን 2017 .

ዋሽንግተን ዲሲ

“እናቴ ሆይ ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ”

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ላይ ተመሥርታለችና ዙሪያዋን በከበቧት ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን መላእክት፣ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ተጋድሎና ጸሎት የታጠረች ናት፡፡ “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤ በተራራ ላይ የተሠራች ከተማ መሰወር አይቻላትም” (ማቴ. ፭፥፲፬) እንዲል መጽሐፍ ቅዱስ ቅዱሳንን በብርሃን ይመስላቸዋል፤ ቅዱሳን ወንጌልን በመስበክ ዓለምን አጣፍጠዋታልና፡፡

ቤተ ክርስቲያን ለእነዚህ ዓለምን ድል ለነሱ ቅዱሳን ከዓመት እስከ ዓመት የተወለዱበትን፣ ተአምራት ያደረጉበትንና ያረፉበትን ቀን አስልታ መታሰቢያቸውን በድምቀት ታከብራለች፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት መካከል ደግሞ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ንጉሡ ለሚያመልከው ጣኦት አንሰግድም በማለታቸው መከራ የተቀበሉበትና በእምነታቸው ጽናት እግዚአብሔርን ደስ በማሰኘታቸው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከነደደው እሳትና የፍላቱ ኃይል ዐሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደ ላይ ከሚዘል የፈላ ውኃ ያዳነበትን ቀን ሐምሌ ፲፱ ቀን አስባ በድምቀት ታከብራለች፡፡

በቤተ ክርስቲያን በየዕለቱ ከሚነበቡ መጻሕፍት መካከልም ስንክሳር ታሪኩን እንዲህ ይተርከዋል፡፡

ቅድስት ኢየሉጣ በሮም ግዛት በሚገኝ አንጌቤን በሚባል አገር በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በክርስትና ሃይማኖት እና በበጎ ምግባር ጸንታ ትኖር የነበረች ደግ ሴት ናት፡፡ በሥርዓት ያሳደገችው ቂርቆስ የሚባል የሦስት ዓመት ሕፃን ልጅም ነበራት፡፡ ይህቺ ቅድስት የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራቷ ከልጇ ጋር ከሮም ወደ ጠርሴስ በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡

የንጉሡ ወታደሮችም እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን አስፈራሯቸው፡፡ ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኃ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡

በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡

አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም “እናቴ ሆይ! ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ” እያለ ቅዱስ ቂርቆስ እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን እንድትጸና አበረታታት፡፡ የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡ እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አስነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲሆን፣ መኰንኑ በተአምራቱ ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡

ዳግመኛም በፈላ የጋን ውኃ ውስጥ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ፤አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ ከፈላ

 ውኃ ያድነናል እያለ ያረጋጋት፣ በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡

ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ውኃውን እንደ ውርጭ አቀዘቀዘው፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ አስገብተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል አድኗቸዋል፡፡ በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡

እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ እያለ በእሳት ውስጥ ሊጣሉ ባሉበት ወቅት እናቱን እንድትጸናና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ሁሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል አይዞህ! አይዞሽ! አትፍራ! አትፍሪ በመባባል በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ ታግሠን፣ እስከ ሞት ድረስ በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር ይገባናል፡፡

ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይሆን በጋራ ዋጋ የሚያገኙበት የድኅነት በር ነውና፡፡ ከዚሁ ሁሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን በተአምኖ ንሴፎ ትንባሌ ዚአከ መዓልተ ወሌሊተ፤ በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡ እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል” ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፴፬፥፯)፡፡ ይህን እንድናደርግም የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡ የቅዱስ ገብርኤል፣ ቅድስት ኢየሉጣ እና ቅዱስ ቂርቆስ ጸሎታቸውና ምልጃቸው ይጠብቀን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ

“ዓላማዬ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችን በዕውቀት ማነጽ ነው” (ሄኖክ ግዛው)

ሄኖክ ግዛው በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የ፳፻፲፯ ዓ.ም ተመራቂ ነው፡፡ በሒሳብ ትምህርት ክፍል አጠቃላይ ውጤት የትምህርት ክፍሉ ሜዳልያና በዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ ውጤት ደግሞ 3.99 በማስመዝገብ በከፍተኛ ውጤት የዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል፡፡ ዩኒቨርሲቲውም በመደበኛ መምህርነት በመቅጥር የሁለተኛ ዲግሪውንም ስፖንሰር በማድረግ እንዲማር ዕደል ሰጥቶታል፡፡

ሄኖክ ይህንን ውጤት እንዴት ማምጣት ቻለ? የቤተሰቦቹና የመምህራኑ ድርሻ ምን ነበር? አስተዳደጉና ለትምህርት የሰጠውን ትኩረት አስመልክተን ከዝግጅት ክፍላችን ጋር ቆይታ አድርጓል፡፡ እንዲህ ተዘጋጅቷል፡፡

ስለ አስተዳደግህ በመግለጽ ውይይታችንን ብንጀምር?

ሄኖክ፡- የተወለድኩት ከወልቂጤ ከተማ 42 ኪሎ ሜትር ርቀት በምትገኘውና ከአበሽጌ ወረዳ ወጣ ብላ በምትገኝ በምዕራብ ሸዋ ዞን ገጠር ቀበሌ ውስጥ ነው፡፡ እንደማንኛውም የገጠር ልጅ ለቤተሰብ እየታዘዝኩ፣ ከብቶች እየጠበቅሁና እያሰማራሁ ነው እስከ ዘጠኝ ዓመቴ ያደግሁት፡፡ ትምህርቴንም በሚመለከት አባቴ እስከ ስምንተኛ ክፍል ተምሮ የነበረ ቢሆንም ቤተሰብን ለመርዳትና ራሱንም ለመቻል ወደ ግብርናው ተሰማርቶና ትዳር ይዞ ኖረ፡፡ ነገር ግን ከፍተኛ ቁጭት ስለነበረው የትምህርት እልሁን በእኛ በልጆቹ መወጣት ይፈልግ ነበር፡፡ በአካባቢያችን ጥሩ ትምህርት ቤት ስላልነበረ ታላቅ ወንድሜን አስቀድሞ ወደ ወደ አበሽጌ ከተማ ልኮ ያስተምረው ስለነበር እኔንም ከወንድሜ ጋር ትምህርቴን እንድከታተል ወደ አበሽጌ ላከኝ፡፡ በየሳምንቱ ዓርብ ለሳምንት የሚሆነን ምግብ ይላክልናል፤ የእኛ ድርሻ መማር ብቻ ነበር፡፡

ለትምህርት የነበረህ ፍላጎትና ውጤትህ ቤተሰቦችህ ላይ ያሳደረው ተጽዕኖ አልነበረም?

ሄኖክ፡- ለታናናሾቼ አርአያ ሆኛለሁ ማለት እችላለሁ፤ እኔን ተከትለው እነርሱም ከፍተኛ የትምህርት ፍቅር አላቸው፡፡ እኔ ደግሞ የታላቅ ወንድሜ ውጤታማነት አግዞኛል፤ እኔም በተፈጥሮ የነገሩኝን ነገር ያለመርሳት፣ በትምህርቴም ክፍል ውስጥ አስተማሪዎቼ ሲያስረዱ የመቀበል አቅም ነበረኝ፡፡ በውጤቴም እስከ መጨረሻው ድረስ የደረጃ ተማሪ ነበርኩ፡፡ ስምንተኛ ክፍልንም 100 ውጤት አምጥቼ ዘጠነኛ ክፍልን ለመማር ወደ ወልቂጤ ከተማ መጣሁ፡፡ ወልቂጤም ብዙ አልተቸገርኩም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ተከታትዬ በጥሩ ውጤት ነው ያለፍኩት፡፡ እናትና አባቴ አንዲት እኅትና አራት ወንድ ልጆችን ነው የወለዱት፡፡ ታላቅ ወንድሜ ከኮሌጅ ተመርቆ አዲስ አባባ ሥራ ላይ ነው፣ እኔ እግዚአብሔር ፈቅዶ ዘንድሮ ተመርቄያለሁ፣ ታናሽ ወንድሜ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሦስተኛ ዓመት አርክቴክቸር ተማሪ ሲሆን ትንሹም በትምህርት ላይ ይገኛል፡፡ አንዲት ታላቅ እኅት ነበረችን እርሷም ትታመም ስለነበር ጸበል በሄደችበት ነው ያረፈችውና ከባድ ኀዘን ነበር በቤታችን ውስጥ የተፈጠረው፡፡

ከቤተሰቦቼ ጋር በጣም የጠበቀ ቅርበት ስለነበረኝ አቅማቸው በፈቀደ መጠን ከማበረታታት ወደኋላ አላሉም፡፡ በተለይ አባታችን ተምራችሁ አንድ ደረጃ ላይ መድረስ አለባችሁ እያለ ስለሚመክረን የቅርብ ክትትሉ አልተለየንም፡፡   

በሰንበት ትምህርት ቤት ስለነበረህ ተሳትፎ ብትገልጽልን? 

ሄኖክ፡- ቤተ ክርስቲያን ከጓደኞቼ ጋር እሄዳለሁ፣ በሰንበት ትምህርት ቤትም በአባልነት ወጣ ገባ ያለ ተሳትፎ ብቻ ነበር የነበረኝ፡፡ እንደ ወጣት ዓለም ስባ እንድታስቀረኝ ዕድሉን አልሰጠኋትም፤ እምነቴን ለመጠበቅ ጥረት እያደረግሁ ነው ያደግሁት፡፡ መውደቅ መነሣቱ ቢኖርም በእምነት ጸንቼ ለመኖር የምችለውን ሁሉ ሳደርግ ነበር፡፡ ወደ አገልግሎት የመግባት ዕድሉን ግን አላገኘሁም፡፡ በተፈጥሮ ዝምታን ስለማበዛ ራሴን ለመማር እንጂ ለማገልገል አላዘጋጀሁትም፡፡  

ከፍተኛ ትምህርት ተቋም (ዩኒቨርሲቲ) ስትገባ መንፈሳዊ ሕይወትህን እንዴት ትመራ ነበር?

ሄኖክ፡- በግቢ ጉባኤ ውስጥ በአባልነት ስሳተፍ ነበር፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ መጸለይ አዘወትራለሁ፡፡ አገልግሎትን በተመለከተ ግን ኮርስ መከታተልና በልዩ ዝግጅት ከመሳተፍ ውጪ ወደ አገልግሎት አልገባሁም፡፡

ቤተሰብ ውጤታማ ሆነህ እንድትወጣ ከመጓጓትና ለትምህርትህ ልዩ ትኩረት እንድትሰጥ ከመፈለግ አንጻር ወደ ግቢ ጉባኤ እንዳትሄድ አልተከለከልክም?

ሄኖክ፡- ቤተሰቦቼ ለትምህርት ልዩ ትኩረት እንደምሰጥ ስለሚያውቁ ወደ ቤተ ክርስቲንና ግቢ ጉባኤ እንዳልገባ ያደረጉት ጫና አልነበረም፡፡ እኔም ይህንን ስለምረዳ መቼ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ መቼ ግቢ ጉባኤ መሄድ እንዳለብኝ ስለማውቅ ሁሉንም አጣጥሜ ለመጓዝ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡

የትምህርት ክፍሌ (የሒሳብ ትምህርት) ልዩ ትኩረት የሚሻ የትምህርት ዓይነት በመሆኑ ከመምህራን ከማገኘው ዕውቀት በተጨማሪ በራሴም ከፍተኛ ጥረት ሳደርግ ነበር፡፡ የመምህራኖቼም ጥሩ ድጋፍና አይዞህ ባይነት አልተለየኝም ነበር፡፡    

የውጤታማነትህ ምሥጢር ምንድነው?

ሄኖክ፡- የመጀመሪያው ውሳኔ ነው፡፡ በዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ ከተሰጡት 50 የትምህርት ዓይነቶች 43A+ ነውያመጣሁት፣ ከአንድ ትምህርት A-ውጪቀሪዎቹ A ነው ያስመዘገብኩት፡፡ማንኛውም ቤተሰብ ልጆቹ ተምረው ዶክተር እንዲሆኑ ነው የሚመኘው፡፡ ልጆችም ብንሆን ከልጅነት ጀምሮ ዶክተር ወይም አውሮፕላን አብራሪ እንድንሆን እንመኛለን፡፡ እኔ ግን መምህርነትን ከልጅነቴ ጀምሮ ነው ስመኘው የኖርኩት፤ ቤተሰብም ሲጠይቀኝ መምህር ነው የምሆነው ስለምላቸው በውሳኔዬ ነው የጸናሁት፡፡ የመጀመሪያ ዓመት ውጤቴም ከፍተኛ ስለነበረ ለምን ሕክምና አታጠናም የሚሉኝ ብዙዎች ነበሩ፡፡ እኔ ግን ፍላጎቴ ስላልነበር ተማሪዎች የትምህርት ክፍላቸውን ሲመርጡ እኔ ግን ሐሳቤን እንዳልቀይር ግቢውን ትቼ በመውጣት ወደ ቤተ ክርስቲያን ነው የሄድኩት፡፡ 

ከግቢው ከፍተኛ ውጤት ማምጣት አለብኝ ብዬ አልነበረም የማጠናው፡፡ ነገር ግን በሂደት ጥሩ ውጤት እያመጣሁ መሆኔን ስረዳ ነው በጥሩ ውጤት ተመርቆ የመውጣት ፍላጎቴ ከፍ ያለውና ቢያንስ ሜዳልያ ማግኘት አለብኝ የሚለው ፍላጎት ያደረብኝ፡፡ የጓደኛ ግፊት፣ ሌሎች ሱሶች የሚያጠቁኝ ሰው አይደለሁም፤ ከዓላማዬ የሚያዘናጋኝም የተለየ ችግር ስላልነበር ሙሉ ትኩረቴን ትምህርቴ ላይ ነበር የማሳርፈው፡፡ 

ፈተና ሲኖርም ጠለቅ ያለ ጥናቴን በሦስት ቀን ውስጥ አጠናቅቃለሁ፤ ክፍል ውስጥ የሚሰጠውን ትምህርት በትኩረት እከታተላለሁ፤ አንድ ጊዜ ከተረዳሁ ደግሞ አልረሳም፣ በዚህ ላይ የሒሳብ ትምህርት ክፍል መምህራኖቼ ድጋፍ ስለማይለየኝ በውጤት መዋዠቅ ውስጥ ሳልገባ እስከ መጨረሻው መዝለቅ ችያለሁ፡፡ 

ለጥናት የትኛውን ጊዜ ትመርጥ ነበር?

ሄኖክ፡- ከሰኞ እስከ ዓርብ ጠዋትና ከሰዓት በኋላ ትምህርት ስለሚኖረን ለጥናት ያለኝ ጊዜ ማታ ነው፡፡ ስለዚህ ከራት በኋላ ያለውን ጊዜ ነው የምጠቀመው፡፡ ራት ከበላሁ በኋላ ቢበዛ እስከ ሌሊቱ ሰባትና ስምንት ሰዓት እያጠናሁ ልቆይ እችላለሁ፡፡ ይህ ሰዓት ለእኔ ልዩ ምቾት የሚሰጠኝ ጊዜ ነው፡፡  

ጊዜህን ለትምህርትህ እንደሰጠህ ሁሉ በትርፍ ሰዓትህ በምን ትዝናና ነበር?

ሄኖክ፡- ትርፍ ሰዓት ሲኖረኝ ቀድሞ ሙዚቃ ነበር የማደምጠው ግቢ ከገባሁ በኋላ ግን ከቀድሞ ይልቅ ይበልጥ ቤተ ክርስቲያንን እያወቅኋት በመምጣቴ መዝሙር በመስማት፣ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ነው የማሳልፈው፡፡

በትምህርትህ ውጤታማ እንድትሆን የቤተሰብ ድጋፍ እንዴት ነበር?

ሄኖክ፡- ቤተሰቦቼ በመካከለኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ ናቸው፡፡ ገንዘብም ቢሆን የሚያስፈልገኝን ሁሉ በማሟላት ሲደጉሙኝ ቆይተዋል፡፡ አባቴ ለትምህርት ከተባለ ያለምንም ቅሬታ የቻለውን መሥዋዕትነት ይከፍላል፣ የጠየቅነውን ሳያሟላ ዕረፍት አይኖረውም፡፡ ስለዚህ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ውስጥ ሆኜ ቤተሰቦቼ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ አላሉም፡፡ እኔም አደራቸውን ለመወጣት የቻልኩትን ሁሉ ለማድረግ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡   

አባቴ ለትምህርት ያለው ፍቅር ከፍተኛ ስለሆነና እርሱ ያጣውን በልጆቹ መበቀል ስለሚፈልግ “ከእኔ ምንም አትጠብቁ፣ የማወርሳችሁም ነገር የለኝም፤ ስለዚህ ጠንክራችሁ ተማሩ” በማለት ከፍተኛ ግፊት ስለሚያደርግ ለትምህርት ከሆነ ማንኛውንም መሥዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ የሆነ ቆራጥ አባት ነበር፡፡ ወላጅ እናቴም ከአባቴ የተለየ አመለካከት አልነበራትም፡፡ ለራሳቸው እያስፈለጋቸው አጉድለው ለእኛ ለልጆቻቸው የሚያደረጉት ነገር ያስገርመኛል፡፡ ሁል ጊዜም ከራሳቸው ይልቅ እኛን ያስቀድማሉ፡፡ እዚህ ደረጃ ላይ ለመድረሴ የወላጆቼ ክትትልና ድጋፍ ከፍተኛ ድርሻ ነበረው፡፡

በግቢ ቆይታህ ከጓደኞችህ ጋር ምን ዓይነት ግንኙነት ነበረህ?

ሄኖክ፡- እኔ ጓደኛ ከማያበዙት ወገን ነኝ፡፡ በማደሪያ ክፍላችን ውስጥ አብረን ስላለን አንዳንድ ነገሮችን ልንነጋገር፣ ልንደጋገፍ እንችላለን፡፡ ያ ግንኙነት ጓደኝነት ነው ማለት አይደለም፡፡ ክፍል ውስጥም እንዲሁ፡፡ ነገር ግን ትምህርቴን ጨርሼ ከግቢ እስክወጣ ድረስ አንድ ጓደኛ ብቻ ነበረኝ፡፡ ከእርሱም ጋር ትርፍ ሰዓት ካለን ነው የምንገናኘው፤ በተለይ ቅዳሜ ከቅዳሴ በኋላ ጊዜ ስለሚኖረን አብረን እንሆናለን፣ ሻይ ቡና እንላለን፡፡ በግል ሕይወታችን ዙሪያም እንመካከራለን፡፡ በተረፈ ቀሪውን ሰዓት ደግሞ ዕረፍት አደርጋለሁ፡፡

ከክፍል ልጆች ጋር ደግሞ ፈተና ከመድረሱ በፊት አስረዳን ስለሚሉኝ ባዶ ክፍል ፈልገን አስረዳቸዋለሁ፣ እኔም እያስረዳሁ አብሬ እማር ነበር ማለት እችላለሁ፡፡

በግቢ የነበረህ ቆይታ በድል ተወጥተኸዋልና የወደፊት ዓላማህ ምንድነው?

ሄኖክ፡- ተቋሙ የመምህርነት ዕድሉን ሰጥቶኛል፣ በዚህ ላይ ደግሞ ሁለተኛ ዲግሪዬን እንድማር ስፖንሰር ሆኖኛል፡፡ የወደፊት ዕቅዴ በመምህርነቱ የመቀጠል ፍላጎት ቢኖረኝም ግቢ ውስጥ ለረጅም ጊዜ የመቆየት ፍላጎት የለኝም፡፡ ከታች ወርጄ አንደኛ ወይም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ ለማስተማር ነው የማስበው፡፡ ዓላማዬ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችን በዕውቀት ማናጽ ነው፤የትምህርት መሠረት የሚገነባው ከሕፃንነት ጀምሮ ነውና ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ የድርሻዬን መወጣት አለብኝ፡፡ በማኅበረሰብ አገልግሎትም የመሳተፍ ፍላጎት ስላለኝ ይህንን ሕልሜን ለማሳካት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ ልጆቹን መንገድ ማሳየት፣ መምራት ላይ ትኩረት አደርጋለሁ፡፡ እዚሁ ወልቂጤ እያስተማርኩም ታናናሽ ሁለቱን ወንድሞቼን ማስተማር፣ አብሬአቸው መኖርና ውጤታማ ይሆኑ ዘንድ መርዳት እንዳለብኝ ራሴን አሳምኜዋለሁ፡፡

በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እና በመንፈሳዊ ሕይወት ጸንቶ ለመኖር የምታደርገው ጥረት ምን ይመስላል?

ሄኖክ፡- ከልጅነቴ ጀምሮ ከተሳታፊነት ባለፈ ደፍሮ ወደ አገልግሎት የመግባት ልምዱ የለኝም፡፡ ጸጋውም ያለኝ አይመስለኝም፡፡ ነገር ግን ያለ መንፈሳዊ ሕይወት ትርጉም አይኖረውምና ጥሩ ክርስቲያን መሆን፣ ቤተሰቤንም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ተገንዝበው በመልካም መንገድ ላይ እንዲጓዙ አርአያ መሆን እፈልጋለሁ፡፡

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ተማሪዎች በመደበኛ ትምህርታቸውም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ ከተሞክሮህ በመነሣት ልምድህን ብታካፍል?

ሄኖክ፡- የገጠር ወይም የከተማ ልጅ ብሎ መከፋፈሉ አስፈላጊ ባይሆንም እስከሚለምዱት ድረስ ጫናው በገጠር ልጆች ላይ የሚበረታ ይመስለኛል፡፡ እኔም የተገኘሁት ከገጠር ስለሆነ ስሜታቸውን እጋራለሁ፡፡ ማንኛውም ተማሪ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሲገባ ግር ሊለው ይችላል፡፡ የመደናገጥ፣ ፍርሃት ውስጥ የመግባት ችግር ሊገጥመው ይችላል፡፡ ነገር ግን ይህንን በመቋቋም ከማንም እንደማያንስና የተሻለ ብቃት እንዳለው በማመን ተስፋ ሳይቆርጥ መማር ይገባዋል፡፡

ትምህርት ጊዜን ይፈልጋል፣ ለፈተና ብቻ ብለን የምናጠናው ሳይሆን ዕውቀታችን ለማስፋት፣ ወደፊት ለሚጠብቀን የሕይወት ምዕራፍ እንደሚረዳን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ከማኅበራዊ ሚዲያ ጋር ያላቸውን ቁርኝት መቀነስ፣ ሞባይላቸውን ለትምህርት አጋዥ ለሚሆኑ አገልግሎቶች ብቻ ማዋል ይጠበቅባቸዋል፡፡ ማኅበራዊ ሚዲያው ብዙዎችን ከዓላማቸው እያዘናጋ ያሰቡበት እንዳይደርሱ እንቅፋት ስለሚሆን ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ተሞክሮህን ስላካፈልከን በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ሄኖክ፡- እኔም አመሰግናለሁ፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ማስታወቂያ

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ አገልግሎቱን በማጠናከር በግቢ ጉባኤያት ላይ ውጤታማ ሥራ ለመሥራትና ብቁ አገልጋዮችን ለማፍራት ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ ፕሮጀክቶቹን ለማስፈጸም ይረዳውም ዘንድ ልዩ የገቢ ማሰባሰቢያ ትኬት ሽያጭ ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በማሠራጨት ላይ ይገኛል፡፡ እርስዎም ትኬቱን በመግዛት ትውልድን ለመቅረጽ በሚደረገው ጥረት ውስጥ አሻራዎን ያኑሩ፡፡

ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወቅዱስ ጳውሎስ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርታ የሚነበበውን ምንባብ፣ የሚዘመን ዜማ በቀለም ለይታ ሐምሌ ፭ ቀን ከዋዜማው ጀምሮ በታላቅ ድምቀት በዓላቸውን ከምታከብላቸው ሐዋርያት መካከል የሊቀ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ ዕረፍት አንዱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በምድር ላይ ሳሉ እግዚአብሔርን አምነው፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ቃል አስገዝተው ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ድውያንን እየፈወሱ፣ በየደረሱበት ቃለ እግዚአብሔርን ለተራቡና ለተጠሙ ምእመናን በመመገብና በማጠጣት በሚታወቁ ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን የተከበበች ናት፡፡ ታሪካቸውንም ሰንዳ ለትውልድ በማስተላለፍ ብቸኛዋ ተቋም ናት፡፡ 

የሐዋርያትን ታሪክ ለማወቅ ዋናው ምንጩ የቤተ ክርስቲያን የታሪክ መጻሕፍት ናቸው። በዚህም መሠረት በቤተ ክርስቲያናችን ሐምሌ ፭ ቀን በዓላቸውን ከምታከብርላቸው ሐዋርያት መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ታሪክ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በገሊላ ቤተ ሳይዳ ሲሆን እናቱ ባወጣችለት ስም ስምኦን እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ በጐልማሳነቱ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ተሠማራ። በ፶፭ ዓመት ዕድሜውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዝሙርነት ጠርቶታል፡፡ “በገሊላ ባሕር ዳር ሲመላለስም ሁለቱን ወንድማማቾች ጴጥሮስንና እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ዓሣ አጥማጆች ነበሩና ጌታችን ኢየሱስም ‘ኑ ተከተሉኝ፤ ሰውን የምታጠምዱ እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፬፥፲፰-፳) መረባቸውንም ትተው ተከተሉት፡፡ ቅዱስ ጰጥሮስ በዚህ መንገድ ነው የተጠራውና ቤተሰቡንና ያለውን ሁሉ ትቶ ጌታችንን የተከተለው፡፡

በቂሳርያ ከተማ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን “እናንተስማን ትሉኛላችሁ? ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ ብፁዕ ነህ፤ በሰማይ ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና፡፡ እኔም እልሃለሁ፡- አንተ ዐለት ነህ፤ በዚያች ዐለት ላይም ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲዖል በሮች አይበረቱባትም” አለው፡፡ ጴጥሮስ የሚለው ስም በላቲን ቋንቋ ዐለት ማለት ነው፤ በአርማይክ ደግሞ ኬፋ ይባላል። (ማቴ. ፲፮፥፲፮) በዐለት ላይ የተመሠረተ ቤት ንፋስ በነፈሰ ጊዜ እንደማይፈርስ ሁሉ በክርስቶስ የተመሠረተችው ቤተ ክርስቲያንም በንፋስ የተመሰለው ዲያብሎስ ዙሪዋን ቢዞርም ለያጠፋት እንደማይችል ያመለክታል፡፡ 

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥብርያዶስ ባሕር ላይ በእግሩ ሲራመድ ተመልክቶ እርሱም ይሄድ ዘንድ ፈቃድ የጠየቀ፣ መሄድ የጀመረና ማዕበሉን ፈርቶም የተጠራጠረ፣ በዚህም ምክንያት ለመስጠም የደረሰ፣ ጌታችንን ያድነው ዘንድ የተማጸነ፣ ጌታችንም በጥያቄው መሠረት ከመስጠም ያዳነው እንደሆነ ቅዱስ ወንጌል ያስተምረናል፡፡ (ማቴ. ፲፬፥፳፪-፴፫)

በቅፍርናሆም ጉባኤ ጌታን ምሥጢረ ቁርባንን ሲያስተምር አይሁድ ስላልገባቸው ወደ ኋላ አፈገፈጉ። “እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላችሁ?” ብሎ ጌታችን ሐዋርያትን ጠየቃቸው። “ጌታ ሆይ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም የሕይወት ቃል አለህ። እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ እናምናለን” በማለት ሐዋርያትን ወክሎ የመለሰ እርሱ ነው። (ዮሐ. ፮፥፷፮-፷፰)

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እረኛው መሞትና ስለ በጎቹ መበተን ሲያስተምር ለደቀ መዛሙርቱ “በዚህች ሌሊት ሁላችሁም ትክኛላችሁ” ብሎ በተናገረ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ “ሁሉም ቢክዱህ እንኳ እኔ ከቶ አልክድህም” (ማቴ. ፳፮፥፴፬) ብሎ ተናግሯል፡፡ ነገር ግን በዚያው ሌሊት ጌታችን በአይሁድ በምቀኝነት ይሰቅሉት ዘንድ በተያዘ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አስቀድሞ የተናገረውን ቃል ዘንግቶ ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ ክዶታል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ የሚታወቅበት ሌላው ትልቁ ነገር ንስሓው ነው። አምላኩን መበደሉን ሲረዳ ተጸጽቶ ምርር ብሎ የንስሓ ዕንባን አንብቷል፡፡ 

በበዓለ ሃምሳ ለደቀ መዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ ለተሰበሰቡት አይሁድ ወንጌልን የሰበከ፣ ሦስት ሺህ ምእመናንን አሳምኖ የመጀመሪያዋን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የመሠረተ እርሱ ነው። (የሐዋ. ፩፥፲፮-፳፫ ፤ ፪፥፲፬-፴) ልዑል እግዚአብሔር ባደለው ጸጋ ጥላው እንኳን ድውያንን ይፈውስ ነበር። (ሐዋ.  ፭፥፲፭)።

ቅዱስ ጴጥሮስ  በፍልስጥኤም፣  በሶርያ፣  በጳንጦን፣  በገላትያ፣  በቀጰዶቅያ፣ በቢታንያ እና በሮሜ ሰብኳል። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በሮሜ አንድ ዓመት ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ካስተማረ በኋላ የሮሜ ክርስቲያኖች እየበዙ ከመምጣታቸውም በላይ የክርስትናው ጉዞ እስከ ሮማ ባለሥልጣናት ደረሰ። የኔሮን የቅርብ ባለሥልጣናት የሆኑት የአልቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች ወደ ክርስትናው ገቡ። በዚህን ጊዜ ኔሮን ንጉሠ ሮማ በቅንዓት ተነሣባቸው።

ኔሮን በሮም የነገሠው በ፶፬ ዓ.ም. ነው። በመንግሥቱ መጀመሪያ ደግ ሰው ነበረ። ነገር ግን በነገሠ በዓመቱ የጨካኝነት ዐመሉ ብቅ ማለት ጀመረ እና የአባቱን ልጅ አስገደለ። በ፶፱ ዓ.ም. ደግሞ እናቱን በመርዝ ገደለ። በ፷፫ ዓ.ም. እያስተማረ ያሰደገውን መምህሩን ፣ በ፷፪ ዓ.ም. የልጅነት ሚስቱን አግታሺያን አስገደለ። ከእርስዋ በኋላ ያገባትን ሚስቱንም ፓፒያን ገደላት። በ፷፬ ዓ.ም ከከተማው ወጣ ብሎ በሚገኘው ቤተ መንግሥቱ ተቀምጦ የሮማን ከተማ እሳት ለቀቀባት። የሮም ሕዝብ በደረሰው አደጋ እጅጉን ተቆጣ። ኔሮንም በክርስቲያኖች አመካኘ። በዚህም የተነሣ በሮማ ከተማ ሁለት ዓይነት ወሬ መናፈስ ጀመረ።

የሮማ አማልክት በክርስቲያኖች ሃይማኖት ስለተቆጡ በከተማዋ እሳት አዘነቡባት የሚለው የመጀመሪያው ሲሆን ክርስቲያኖች ሆን ብለው ከተማዋን አቃጥለዋታል የሚለው ደግሞ ሁለተኛው ወሬ ነበር። የከተማው መጋየት ያበሳጨው የሮማ ሕዝብ፣ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ እያወጣ መግደሉን ተያያዘው። ይህን የሰሙት የአግቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች (የሮም ባለሟሎች ነበሩ) “አንተ ትረፍልን” ብለው በከተማዋ ግንብ በገመድ አሥረው በቅርጫት በማውረድ ቅጥረ ሮማን ለቅቆ እንዲወጣ አደረጉት።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በኦፒየም ጎዳና ጉዞውን ቀጠለ። ሮማን ለቀቀ። እያዘገመ በሸመገለ ጉልበቱ ሲጓዝ አንድ ቀይ ጐልማሳ ወደ እርሱ ሲመጣ አየ። እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን መሆኑን ተረዳ። ወዲያው በፊቱ ተደፋና “ጌታዬ ወዴት እየተጓዝክ ነው?” አለና ጠየቀው። “ዳግም በሮም ልሰቀል” አለው። በዚህ ሰዓት ቅዱስ ጴጥሮስ አዘነና እንደገና ወደ ሮም ተመለሰ። የኔሮን ወታደሮች እየፈለጉት ነበር። “እነሆኝ ስቀሉኝ” አለ ቅዱስ ጴጥሮስ። ያን ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስን ይዘው አሠሩት። ከጥቂት ቀናት በኋላም ሮማውያን የመስቀያውን እንጨት አቀረቡለት። ያን ጊዜ “እኔ እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም” በማለት ቁልቁል እንዲሰቅሉት ለመነ። እንደለመነውም ሐምሌ ፭ ቀን ፷፯ ዓ.ም ቁልቁል ሰቅለውት በሰማዕትነት ዐረፈ።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዘሩ ከዕብራዊያን፣ ከብንያም ነገድ ሲሆን የተወለደውም በጠርሴስ ከተማ ነው። ጠርሴስ በንግድዋ የታወቀች የኪልቂያ ዋና ከተማ ናት። በከተማዋ እስከ አምስት መቶ ሺህ የሚገመቱ ከየሀገሩ የተሰባሰቡ ሕዝቦች ነበሩባት። ሮማውያን በሥራቸው ለሚተዳደሩት ሕዝቦች ሮማዊ ዜግነትን ይሰጡ ስለነበር፥ የቅዱስ ጳውሎስ አባት በዜግነት ሮማዊ ነበር። ይህም ለቅዱስ ጳውሎስ ተላልፎለታል።

ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ከታወቀው የገማልያል ትምህርት ቤት ገባ። በዚያም የአይሁድን ሕግና ሥርዓት እየተማረ እስከ ፴ ዓመቱ ቆየ። በ፴ ዓመቱ የአይሁድ ሸንጎ አባል ሆኖ ተቆጠረ።ለኦሪታዊ እምነቱም ቀናተኛ በመሆኑ ክርስቲያኖችን ያሳድድ ነበር። ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ ተከሶ በአይሁድ ሸንጎ ፊት በቀረበ ጊዜ በድንጋይ ተወግሮ በሰማዕትነት ሲያርፍ የወጋሪዎችን ልብስ በመጠበቅ የተባበረ ነው። “ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስን በገደሉትም ጊዜ እኔ እዚያ አብረአቸው ነበርሁ፤ የገዳዮችንም ልብስ እጠብቅ ነበር” እንዲል፡፡ (ሐዋ. ፳፪፥፳)

ቅዱስ ጳውሎስ በደማስቆ ከተማ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን ሲሰማ ወደ ሊቀ ካህናቱ ቀርቦ ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የሚያስችለውን የፈቃድ ደብዳቤ አገኘ። ከዚህም በኋላ ጭፍሮችን አስከትሎ ወደ ደማስቆ አመራ። ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ከተማዋ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ነበር ከሰማይ የወረደው ብርሃን አካባቢውን ያለበሰውና “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚለውን ድምፅ የሰማው። ሐዋርያው ጳውሎስም “ጌታ ሆይ ማን ነህ?” ብሎ ጠየቀ። “አንተ የምታሳድደኝ እኔ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ። የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል” ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናገረው። ያን ጊዜም በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ “ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?” ሲል ጠየቀ። ከዚህ በኋላ ተነሥቶ ወደ ደማስቆ እንዲገባ ተነገረው። ነገር ግን ዓይኖቹ ማየት አልቻሉም፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ ሐናንያ ወደሚባል ሰው ወሰዱት፡፡ ሐናንያም እጁን ጭኖ ጸለየ፡፡ ከዓይኖቹም እንደ ቅርፊት ያለ ነገር ተገፎ ወደቀለት፣ ዓይኖቹም ተገለጡ፣ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ ስለ ጌታችንም “የእግዚአብሔር ልጅ ነው” በማለት መስበኩን ቀጠለ፡፡ (የሐዋ. ፱፥፩-፲፰)

አይሁድም ቅዱስ ጳውሎስን ይገድሉት ተነሡ። ሐዋርያት ግን የቅዱስ ጳውሎስን መመለስ ለማመን ቢቸገሩም በርናባስ ወስዶ የጳውሎስን መመለስ በመተረክ እንዲያምኑት አደረጋቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጠርሴስ ከተማ ለዘጠኝ ዓመታት ቆይቷል። ከኢየሩሳሌም ውጭ የአሕዛብ ከተማ በነበረችው በአንጾኪያ የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፋ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመጀመሪያው ጉዞ ያደረገው ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ጥሪ በአሕዛብ ሀገር ወንጌልን ለመስበክ ከበርናባስ ጋር ወጡ። በዚህ ጉዞአቸው በጠቅላላው ወደ ሁለት ሺህ ኪሎ ሜትር የሚደርስ መንገድ በእግር ተጉዟል። ይህም ጉዞ የተከናወነው በ፵፮ ዓ.ም. አካባቢ ነው። የተሸፈኑትም ሀገሮች ሲሊንውቂያ፣ ቆጵሮስ፣ ስልማን፣ ጳፋ፣ ጰርጌን፣ ገላትያ፣ ጵስድያ፣ ኢቆንዮን፣ ሊቃኦንያ፣ ልስጥራ፣ደርቤን፣ጵንፍልያ፣አታልያና አንጾኪያ ናቸው።

ሁለተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶ ዓ.ም. ገደማ ነው። በመጀመሪያው ጉዞ ማርቆስ አብሮ ተጉዞ ነበር። ነገር ግን ጵንፍልያ ከተማ ሲደርስ እናቱ ስለናፈቀችው መመለስ በመፈለጉ በርናባስ ወደ ኢየሩሳሌም ይዞት መጣ። ስለዚህም በሁለተኛው ጉዞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲላስን ይዞ ወደ ኪልቂያ ሶርያ ሲጓዝ በርናባስ ደግሞ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ ሄደ። በዚህ ጉዞው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ግሪክ ደርሶአል። የተጓዘባቸውና ያስተማረባቸው ከተሞችም፦ ደርብያ፣ ልስጥራ፣ፍርግያ፣ ገላትያ፣ ሚስያ፣ጢሮአዳ፣ ሳሞትራቄ፣ ናፑሊ፣ ፊልጵስዩስ፣ ተሰሎንቄ፣ በርያ፣አቴና፣ ቆሮንቶስ፣ አንክራኦስ፣ አፌሶን፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌምና አንጾኪያ ናቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ያገኘው በዚሁ ጉዞው በልስጥራ ከተማ ነው።

ሦስተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶፬ ዓ.ም. ሲሆን የተሸፈኑትም ሀገሮች የሚከተሉት ነበሩ። ገላትያ፣ ፍርግያ፣ ኤፌሶን፣ መቄዶንያ፣ ፊልጵስዩስ፣ ቆሮንቶስ፣ ጢሮአዳ፣ አሶን፣ ሚልጢኒን፣ አንጠቀከስዩ፣ ትሮጊሊዩም፣ መስጡ፣ ቆስ፣ ሩድ፣ ጳጥራ፣ ጢሮስ፣ ጵቶልማይስ፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም ናቸው።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከልዩ ልዩ ሀገሮች ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ዕርዳታ ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን በመያዝ ሦስተኛውን ጉዞ አጠናቅቆ ኢየሩሳሌም ገባ። ነገር ግን ኢየሩሳሌም የገባበት ጊዜ የፋሲካ በዓል ስለነበር ከልዩ ልዩ ሀገሮች የተሰበሰቡ አይሁድ በከተማዋ ነበሩ። እነዚህ በዝርወት የሚኖሩ አይሁድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በየሀገራቸው በትምህርቱ የተነሣ ሲቃወሙት የነበሩ ናቸው።

መስበኩን በመቀጠሉ ምክንያት በ፶፰ ዓ.ም በሮም ለቁም እሥር ተዳረገ። የሁለቱን ዓመት የቁም እሥር እንደጨረሰ ወደ ኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ። ይህም በ፷ዎቹ ዓ.ም ነው። በፍርድ ቤቱ በተደረገው ምርመራ የሮሜን ሕግ የሚቃወም ምንም ወንጀል ስላልተገኘበት በነፃ ተለቀቀ፤ ከዚህ በኋላ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አራተኛውንና የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያልመዘገበውን ጉዞውን ያደረገው። ይህ ጉዞው በመታሠሩ አዝነው ተክዘው የነበሩ ክርስቲያኖችን ለማጽናናት የጀመራቸውን ሥራዎች ፍጻሜ ለማየት የተደረገ ጉዞ ነው። በዚህም ጉዞው ኢየሩሳሌምን፣ ኤፌሶንን፣ ሎዶቅያን፣ መቄዶንያን፣ ቀርጤስን፣ ጢሮአዳን፣ ድልማጥያን፣ እልዋሪቆን፣ ኒቆጵልዮን፣ ብረንዲስን፣ ጎብኝቷል። በዚህ የመጨረሻ የስብከት ጉዞው ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል።

በመጨረሻ በ፷፬ ዓ.ም. ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ምን እንደምትመስል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት። የሮም ሕዝብ በከተማው መቃጠል በማዘኑና በማመፁ ነገሩን ሁሉ በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ። በዚህም የተነሣ ክርስቲያን የተባለ ሁሉ መሰደድ፣ መሠየፍ፣ መታረድ እጣ ፈንታው ሆነ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኒቆጵልዮን ከተማ ሲያስተምር በ፷፭ ዓ.ም. ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ። ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታሥሮ ከቆየ በኋላ በ፸፬ ዓመት ዕድሜው በሮም ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሰይፎ በ፷፯ ዓ.ም. ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት፣ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ዐስራ አራት መልእክታትን ጽፈዋል። የቅዱሳኑ ሐዋርያት ረድኤትና በረከታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፤ አሜን።

ምንጭ፦ መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ ፭፤ መጽሐፍ ቅዱስ ሐዲስ ኪዳን፣

           ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ ቁጥር ፩፤ በማኅበረ ቅዱሳን