ዳግም ትንሣኤ

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዐርብ ተሰቅሎ፣ በሦስተኛውም ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል በዝግ መቃብር ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣና በትንሣኤው ትንሣኤአችንን ካወጀልን በኋላ ሐዋርያት በአንድነት ተሰብስበው ሳለ ተገልጦላቸዋል፡፡ ይህንንም ወንጌላውያኑ በመተባበር ገልጸውታል፡፡ በተለይ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ “ያም ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን በመሸ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ አይሁድን ስለ ፈሩ ተሰብስበው የነበሩበት ቤት ደጁ ተቆልፎ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ በመካከላቸው ቆመና ‘ሰላም ለእናንተ ይሁን’ አላቸው፡፡ ይህንም ብሎ እጆቹንና ጎኑን አሳያቸው፤ ደቀ መዛሙርቱም ጌታችንን ባዩት ጊዜ ደስ አላቸው” (ዮሐ. ፳፥፲፱-፳፤ ማቴ. ፳፰፥፲፮-፳፤ ሉቃ. ፳፬፥፴፮-፵፱) በማለት ገልጾታል፡፡

ይህ ሁሉ ሲሆን ግን ዲዲሞስ የተባለው ቶማስ አብሯቸው አልነበረምና የሆነውን ቢነግሩት አላምንም አለ፡፡ ይህንንም ወንጌላውያኑ ሲገልጹት “… ጌታችንን አየነው” አሉት፡፡ እርሱ ግን “የችንካሩን ምልክት በእጁ ካላየሁ፤ ጣቱንም ወደተቸነከረበት ካልጨመርሁ፤ እጄንም ወደ ጎኑ ካላስገባሁ አላምንም” አላቸው፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፬-፳፭)፡፡

ከስምንት ቀን በኋላም ሐዋርያት፣ ካላየሁ አላምን ያለው ቶማስን ጨምሮ በአንድነት ተሰብስበው ባሉበት በሩ እንደተዘጋ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ በመካከላቸውም ቆመ፡፡ እንዲህም አላቸው፡- “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡፡” ከዚህም በኋላ ቶማስን “ጣትህን ወዲህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና ወደ ጎኔ አግባ፤ እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን” አለው፡፡ ቶማስም ”ጌታዬ አምላኬም” ብሎ መለሰ፡፡ ጌታችን ኢየሱስም “ስለአየኸኝ አመንህን? ብፁዓንስ ሳያዩ የሚያምኑ ናቸው” አለው፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፮-፳፱)፡፡

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን ዕለት ዳግም ትንሣኤ ብላ ሰይማ ሥርዓቱንም እንደ ትንሣኤው ትፈጽማለች፣ በድምቀት ታከብራለች፡፡

በዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፡-

  • መልእክታት፡- (፩ቆሮ. ፲፭፥፩-፳)
  •                   :- (፩ዮሐ. ፩፥፩- ፍጻሜው)
  • ግብረ ሐዋርያት፡- (ሐዋ. ፳፫፥፩-፲)
  • ወንጌል፡-       (ዮሐ. ፳፲፱-ፍጻሜው)
  • ቅዳሴ፡-         ዲዮስቆሮስ

ከትንሣኤ ማግሥት እሰከ ዳግም ትንሣኤ የቀናት ስያሜዎች

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ማግስት አንሥቶ እስከ የሚቀጥለው እሑድ (ዳግም ትንሣኤ) ያሉትን ቀናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለእያንዳንዳቸው ዕለታት ስያሜ ሰጥታ ታስባቸዋለች፡፡ እነዚህንም ቀጥለን እንመለከታቸዋለን፡፡

፩. የትንሣኤ ማግሥት/ ሰኞ ማዕዶት (ሽግግር) ወይም ፀአተ ሲኦል

ነፍሳት ከሲኦል እሥራት ነጻ መውጣታቸው እንዲሁም ከሞት ወደ ሕይወት መሸጋገራቸው የሚታሰብበት ዕለት ነው፡፡ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለ፶፻፭፻ (አምስት ሺህ አምስት መቶ) ዘመን በሲኦል እስራት፣ በጠላት ዲያቢሎስ ግዛት የነበሩትን ነፍሳት ነጻ አውጥቶ አዳምና ልጆቹን ወደ ቀድሞ ርስታቸው የመለሰበት ዕለት መታሰቢያ ነው፡፡ ይህቺን ዕለት አጥተን የነበረውን ነጻነት ማግኘታችንን፣ ባርነቱ ቀርቶ ዳግመኛ ልጆች መሆናችንን፣ ሰላም ይናፍቁ የነበሩ አዳምና ልጆቹ ሰላማቸው ታውጆ፣ ጭንቀታቸው ርቆ፣ በደስታ ወደ ገነት መመለሳቸውን እናስብበታልን፡፡

፪. ማክሰኞ (ቶማስ)

ጌታችን መነሣቱን ለቅዱሳን ሐዋርያተ በገለጸ ጊዜ በቦታው ሐዋርያ ቶማስ አልነበረምና የጌታንን ትንሣኤ ሲነግሩት ካላየሁ አላምንም በማለቱ ጌታችን እርሱ ባለበት ዳግመኛ ለሐዋርያ ተገለጸ፤ ቅዱስ ቶማስንም … ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንክ እንጂ ያላመንክ አትሁን አለው፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፯) ቅዱስ ቶማስም የእጆቹን ጣቶች ጌታችን በዕለተ ዓርብ ሌንጊኖስ በተባለ ጭፍራ በወጋው ጎኑ ሰደደ፤ የዚህን ጊዜ እጁ ኩምትር አለች፤ ቅዱስ ቶማስም ጌታዬ አምላኬ ብሎ መስክሯል፡፡ የዚህን ድንቅ ተአምራት መታሰቢያ ማክሰኞ ይታሰባል፡፡

፫. ረቡዕ (አልዓዛር)

አልአዛር ማለት እግዚአብሔር ረድቷል ማለት ነው፤ ጌታችን ከሞት ያስነሣው የማርያምና የማርታ ወንድም ነው፤ በቢታንያ ይኖር የነበረው የጌታችን ወዳጅ አልዓዛር ታሞ ሞተ፤ በዚህን ጊዜ ጌታችን በዚያ ሥፍራ አልነበረምና እንደ አምላክነቱ ባለበት ቦታ ሆኖ የወዳጁ አልዓዛርን መሞት ዐወቀ፤ ደቀ መዛሙርቱንም ወዳጃችን አልዓዛር ተኝቷል፤ ላነቃው  እሄዳለሁ አላቸው፤ ወደ ቢታንም መጣ ከሞተ ዐራት ቀን የሆነውን አልዓዛርን ከመቃብር አስነሣው፤ ጌታችን ይህን ድንቅ ተአምር ማድረጉን በዚህ ወቅት ታሰባል፡፡ (ዮሐ. ፲፩፥፲፩-፵፬)

፬. ሐሙስ (አዳም ሐሙስ)

አዳም በበደለ ጊዜ በደሉን አምኖ ንስሓ ገባ፤ ተጸጸተ፤ እግዚአብሔርን መበደሉንና ትእዛዙን መጣሱን አምኖ ለብዙ ዓመት ሲያለቅስ ኖረ፤ ጠላትም አስጨንቆ ገዛው፤ የዕዳ ደብዳቤ አጽፎ አዳም ገብሩ ለዲያቢሎስ፣ ሔዋን ዓመቷ ለዲያቢሎስ የሚል የዕዳ ደብዳቤ አጻፋቸው፤ አዳምም ስለ በደሉ መሥዋዕትን ለእግዚአብሔር አቀረበ፤ ጌታችንም የአዳምን መጸጸትና መመለስ ተቀብሎለት አምስት ሺ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጁ ተወልዶ እንደሚያድነው ቃል ኪዳን ገባለት፤ ይህም ዕለት በዚህ ቀን ይታሰባል፤ አዳም ሐሙስ መባሉ ለዚህ ነው፡፡

፭. ዓርብ (ቅድስት ቤተ ክርስቲያን)

በዚህ ዕለት የሚታሰበው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክቡር ደሙ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንደመሠረተ ነው፡፡ በሐዋርያት ሥራ ላይ  ቅዱስ ሉቃስ …እግዚአብሔር በደሙ የዋጃትን ቤተክርስቲያን ትጠብቁ ዘንድ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመ …” በማለት እንደገለጸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው፡፡ (የሐ. ፳፥፳፰) ይህ ዕለት የዚህ መታሰቢያው ነው፡፡

፮. ቅዳሜ (ቅዱሳን አንስት)

ከመቶ ሃያው ቤተሰብ መካከል ሰላሣ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት ናቸው፤ የትንሣኤውን ብሥራት ሰምተዋልና … መልአኩም መልሶ ሴቶቹን አላቸው፤ እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ አውቃለሁና፤ እንደተናገረ ተነሥቷልና፤ በዚህ የለም የተኛበትን ሥፍራ ኑና እዩ… በፍርሃትና በታላቅ ደስታም ፈጥነው ከመቃብር ሄዱ፤ ለደቀ መዛሙርቱም ሊያወሩ ሮጡ፤ እነሆም ኢየሱስ አገኛቸውና ደስ ይበላችሁ አላቸው እነርሱም ቀርበው ሰገዱለት፡፡… (ማቴ. ፳፰፥፭-፱) ከትንሣኤ በዓል በኋላ ያለው ቅዳሜ የጌታችንን ትንሣኤ ያበሠሩና የመሰከሩ ቅዱሳን አንስት የሚታሰቡበት ዕለት በመሆኑ ቅዱሳን አንስት ይባላል፡፡

እሑድ (ዳግም ትንሣኤ)

ጌታችን ዐሥሩ ደቀ መዛሙርት ባሉበት ቅዱስ ቶማስ ባልነበረበት ተገልጦ ስለነበር ቅዱስ ቶማስ ባለበት በዚህች ዕለት በዝግ ቤት ሳሉ ተገልጾላቸዋል፤ … ከስምንት ቀን በኋላም ደቀ መዛሙርቱ ደግመው በውስጥ ነበሩ፤ ቶማስም ከእነርሱ ጋር ነበረ፤ ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ ቶማስን ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን” አለው፡፡ ቶማስም “ጌታዬ አምላኬ” ብሎ መለሰለት፡፡”” (ዮሐ. ፳፥፳፮-፳፰) በዚህም የተነሣ ይህ ዕለት ዳግም ትንሣኤ ተብሏል፡፡

መልካም ዘመነ ትንሣኤ!

“ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል” (ዮሐ. ፲፩፥፳፭)

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን……. በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን

አሰሮ ለሰይጣን …….. አግዓዞ ለአዳም

ሰላም.. እምይእዜሰ

ኮነ……. ፍሥሓ ወሰላም

ትንሣኤ የሚለው ቃል “ተንሥአ፤ ተነሣ” ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙ መነሣት ማለት ነው፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ሞቶ ሥጋው ፈርሶና በስብሶ እንደማይቀር እና በዳግም ምጽአት ጊዜ እንደሚነሣ የሚያመለክት ነው፡፡ የሰው ልጅ ከፈጣሪ የተሰጠውን ትእዛዝ ባለመጠበቁ ምክንያት የሞት ሞት ተፈርዶበት ነበረ፡፡ “እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ፣ አትንኩትም” ተብሎ ነበርና፡፡ (ዘፍ. ፫፣፫) በዚህም ምክንያት ከአቤል ጀምሮ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ የሰው ልጅ በሥጋ የሚሞት ሆኗል፡፡ ነገር ግን እንደሞትን አንቀርም፡፡ ሁላችንም ትንሣኤ አለን፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣት የትንሣኤያችን በኩር ሆኖናልና፡፡(፩ኛ ቆሮ.፲፭፣፳፩)፡፡

“ሞት በሰው በኩል ስለመጣ ትንሳኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኗል” እንዲል፡፡ ፈርሶ በስብሶ መቅረት የቀረልን አካላዊ ቃል ሥጋችን ተዋሕዶ ሰው ሆኖ ሞትን በሞቱ ድል ከነሣልን በኋላ ነው፡፡ ሊቁ በሃይማኖተ አበው “ሞተ ክርስቶስ በሞተ ዚኣነ ከመ ይቅትሎ ለሞት በሞቱ፤ ሞትን በሞቱ ያጠፋልን ዘንድ ክርስቶስ በተዋሐደው ሥጋ የእኛን ሞት ሞተ” ብሎ እንደገለጠው፡፡ (ዮሐ. ፲፩፣፳፭)

“ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ” ያለ ጌታ በጥንተ ትንሣኤ መጋቢት ፳፱ ቀን በዕለተ እሑድ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ መልአኩም (ማር. ፲፮፣፮) “አትደንግጡ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስ ትሻላችሁን? ተነሥቷል” ብሎ ለቅዱሳት አንስት ነግሯቸዋል፡፡ (ሉቃ. ፳፬፣፮)፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ የተነሣው በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ነው፡፡ የትንሣኤያችን በኩር የሆነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱሰስ ክርስቶስ አዳምና ልጆቹን በገባው ቃል ኪዳን መሠረት አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷም ነፍስን ነሥቶ በድንግልና ተፀንሶ በድንግልና ተወለደ፡፡ በዚህ ምድር ላይም እየተመላለሰ ሕይወት የሆነውን ወንጌልን እያስተማረ ድውያንን እየፈወሰ፣ የተራቡትን እያበላ፣ የተጠሙትን እያጠጣ ሠላሳ ሦስት ከሦስት ወራትን በምድር ላይ ቆየ፡፡

ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ በአይሁድ እጅ በፈቃዱ ራሱን ለመከራ መስቀል አሳልፎ ሰጠ፡፡ ከሞተ በኋላም በመቃብር ውስጥ ሦስት ቀንና ሌሊት ቆይቶ ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፤ ቅዱስ ዳዊት፡- “ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትተዋትም” ያለው ይኽንን ታላቅ ምሥጢር በትንቢት ቃል ሲናገር ነው፡፡ (መዝ ፲፭፥፲)፡፡ በትንሣኤውም ለሰው ልጆች ሁሉ ትንሣኤያችንን አበሠረን፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆላሲስዩስ ምእመናን በላከው መልእክቱ “…እርሱም በሁሉ ፊተኛ ይሆን ዘንድ መጀመሪያ ከሙታንም በኩር ነው…” በማለት ገልጾናል፤ (ቆላ. ፩፥፲፰) አባታችን ቅዱስ ኤጲፋንዮስም እንዲህ አስተምሯል፤ “አንድ ሆነው የሚነሡትን ትንሣኤ ዛሬ ተስፋ ያደርጋሉ፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሙታን ትንሣኤያቸው በኩር ነው፤ ከእንግዲህ ወዲህም ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ የተነሣ እርሱ ነው፤ ዳግመኛ ሞት አያገኘውም፡፡ (ሃይ. አበ. ፶፯፥፭)

በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረው የሰው ልጅም ሞቶ በስብሶ የሚቀር ሳይሆን የክብር ትንሣኤን ያገኛል፡፡ ጌታችን መደኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “…ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል…” በማለት በአማናዊ ቃሉ አስተምሮናልና፡፡ (ዮሐ. ፲፩፥፳፭) የሚያምኑበት የሕይወት ትንሣኤ፣ ለማያምኑበትም ደግሞ የዘለዓለም ፍርድ እንደሚጠብቃቸው ሲገልጽ “በመቃብር ያሉ ሁሉ ቃሉን የሚሰሙባት ጊዜ ትመጣለችና ስለዚህ አታድንቁ፡፡ መልካም የሠሩ ለሕይወት ትንሣኤ፣ ክፉ የሠሩም ለፍርድ ትንሣኤ ይነሣሉ” እንዲል (ዮሐ. ፭፥፳፰)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት

አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር አዳምና ሔዋን በገነት ሳሉ አትብሉ የተባሉትን ዕፀ በለስን ቀጥፈው በመብላታቸው ከገነት ለመባረራቸው ምክንያት ሆነ፡፡ አዳምም ጸጋው በመገፈፉ ምክንያት በገነታ ካሉ ዛፎች መካካል ቅጠል አገልድሞ ተሸሸገ፡፡ አእግዚአብሔር አዳምና ሔዋን ያደረጉት ሁሉ ያውቃልና “አዳም አዳም የት ነህ?” ሲል ተጣርቷል፡፡ አዳም ግን በፈጣሪው ፊት መቆም አልቻለምና ከትእዛዙ ተላልፎ ዕፀ በለስን በልታልና እንደተሸሸገ ተናገረ፡፡ በሔዋን ላይ ጥፋቱን ቢያሽግርም ከመረገም አልዳነም፡፡ “የሚስትህን ቃል ሰምተሃልና ከእርሱ እንዳትበላ ከአዘዝኩህ ከዚያ ዛፍም በልተሃልና ምድር በሥራህ የተረገመች ትሁን፤ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ፤ እሾህና አሜኬላን ታበቅልብሃለች፤ የምድርን ቡቃያ ትበላለህ፤ ወደወጣህባት ምድር እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራህን ትበላለህ፤ አፈር ነህና ወደ አፈርም ትመለሳለህ” (ዘፍ. ፫፥፲፯-፲፱) አለው፡፡

ነገር ግን አዳም የእግዚአብሔርን ትዛዝ ተላልፏልና እያለቀሰ አምላኩን ለመማጸን ሱባኤ ያዘ፡፡ እግዚአብሔርም በአዳም ከልብ መጸጸት ምክንያት “አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም ከልጅ ልጅሀ ተወልጄ አድንሃለሁ” ባለው አምላካዊ ቃሉ መሠረት ጊዜው ሲደርስ ከሦስቱ አካላት አንድ እግዚአብሔር ወልድ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በድንግልና ተፀንሶ በድንግልና ተወለደ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት፤ ትንቢቱም ይፈጸም ዘንድ መከራን ተቀበለ፤ ጲላጦስ በ፫ ሰዓት ይሰቅል ዘንድ ሲፈርድበትም፤ “መስቀሉንም ተሸክሞ በዕብራይስጥ ጎልጎታ ወደ ተባለው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ወጣ” (ዮሐ. ፲፱፥፲፯) የራስ ቅል ስፍራ ቀራንዮ-ጎልጎታ አዳም ዐጽም የተቀበረበት ቦታ ነበር፡፡ በዚያም የአዳም መቃብር የሆነች ዋሻ አለች፤ የመስቀሉንም እንጨት በዚያ በምድር መካከል አይሁዶች ተከሉት፡፡ የአዳም አጽም ቀድሞ ከአዳም ትውልዶች ሲተላለፍ ከኖኅ ደርሷል፤ ኖኅም ወደ መርከብ እንደ ታቦት አስገብቶት በኋላ መልከጼዴቅ ቀብሮታል፡፡ ጌታችንም ከአዳም የራስ ቅል በላይ ሊያድነው መስቀል ተሸከሞ ተንገላታ፤ አይሁድም የቀራንዮን ምራቅ እየተፉበት፣ እየገረፉትና ከፊት ወደ ኋላ ከኋላ ወደፊት እየጣሉት አሰቃዩት፤ ከወደ ጫፍም አደረሱት፤ ሁለቱንም እንጨት አመሳቅለው ዐይኖቹ እያዩ እጆቹንና እግሮቹን ቸነከሩት፤ በዕለተ ዐርብ ቀትር ፮ ሰዓት ላይም ተሰቀለ፡፡

 በሞቱም ሞትን ገደለ፣ በትንሣኤው ለሰው ልጆች ሁሉ ትንሣኤያችንን አበሠረ፡፡ ሲዖልንም በዘበዘ፣ ሰይጣንን አሰረው፣ አዳምንና ልጆቹንም ነጻ አወጣ፡፡   

ዐሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል

በሰሙነ ሕማማት ጠቅለል ባለ መልኩ የምናስባቸው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማት አሥራ ሦስት ናቸው፡፡ እነርሱም አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል ይባላሉ፡፡ ለክርስቲያኖች እነዚህን ሕማማተ መስቀል ማወቅና ዘወትር ማሰብ ተገቢ በመሆኑ እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

፩. ተኰርዖተ ርእስ (ራስና በዘንግ መመታት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን በዘንግ መመታቱንና መቀጥቀጡን የሚገልጥ ነው፡፡ “ተኰርዖት” የሚለው ቃል ኩርዐ – መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ርእስ ደግሞ ራስ ማለት ነው፡፡ አገረ ገዥው ጲላጦስ “እኔ ከዚህ ጻድቅ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ” ብሎ እጁን ከታጠበ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ገርፎ ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች አሳልፎ ሰጥቶት ነበር፡፡ በአይሁድ ሕግ የተገረፈ አይሰቀልም፤ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም፡፡ እርሱ ጲላጦስ ግን ከገረፈው በኋላ፣ የበደል በደል፣ እንዲሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው (ማቴ. ፳፯፤፳፬፤ ማር. ፲፭፥፲፭፤

ሉቃ. ፳፫፥፳፭፤ ዮሐ. ፲፰፥፴፱)


መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተላልፎ ከተሰጠ በኋላ የእሾህ አክሊል ጐንጉነው ራሱ ላይ ደፍተውበታል፡፡ ራሱንም በዘንግ መትተውታል (ማር. ፲፭፥፲፱)፡፡ የሰው ዘር ከአዳም ጀምሮ በጠላቱ በዲያብሎስ በተጐነጐነ የኃጢአት እሾህ ራሱ ተይዞ ነበርና ይህንኑ ለማስወገድ ከሰማይ የወረደ ሰማያዊ የሆነ ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ ተንኮል የተጐነጐነ አክሊለ ሦክ እንደ ዘውድ ደፋ፡፡ በሲዖል ወድቆ በዲያብሎስ ተረግጦ ራሱ የሚቀጠቀጠውን የሰውን ልጅ ለማዳን መድኃኔዓለም ክርስቶስ ራሱን በመቃ ተቀጠቀጠ፡፡ ከራሱ ላይ በሚወርደው ደም ፊቱ ተሸፈነ፡፡
 
፪.
ተፀፍዖ መልታሕት (በጥፊ መመታት)

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጃቸው በደም፣ ጣቶቻቸው በበደል በረከሰ በአይሁድ እጅ በጥፊ መመታቱን የሚገልጥ ነው፡፡ “ተፀፍዖ” የሚለው ቃል ፀፍዐ በጥፊ መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ መልታሕት ደግሞ ፊት ጉንጭ ማለት ነው፡፡ ጌታችን ለሊቀ ካህናት ቀያፋ እውነትን መናገር እንደ ስድብ ተቆጥሮበት መላልሰው ፊቱን በጥፊ መትተውታል፡፡ ፊቱንም በጨርቅ ሸፍነው “ክርስቶስ ሆይ በጥፊ የመታህ ማነው? ትንቢት ተናገርልን” እያሉ ዘብተውበታል፡፡ በጠላት ዲያብሎስ እጅ ወድቆ በነፍሱ ይቀለድበትና ይንገላታ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ብሎ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ ወድቆ ተጐሰመ፤ ተንገላታ፤ በጥፊም ተመታ (ማቴ. ፳፯፥፳፯)፡፡

ጲላጦስ አሳልፎ ከሰጠው በኋላም አክሊለ ሦክ በራሱ ላይ አኑረው ቀይ ልብስ አልብሰው “የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን” እያሉ እየተሳለቁበት በጥፊ መትተውታል (ዮሐ. ፲፱፥፪-፬)፡፡ አላወቁትም እንጂ እርሱ በመንግሥቱ ሽረት፣ በባሕርዩ ሞት የሌለበት የዘለዓለም አምላክ ነው፡፡
 
፫. ወሪቀ ምራቅ (ምራቅ መተፋት)

ርኩሳን አይሁድ በብርሃናዊው የክርስቶስ ፊት ላይ በሚያስጸይፍ ሁኔታ ምራቃቸውን እንደተፉበት የሚገልጥ ነው፡፡ “ወሪቅ” የሚለው ቃል ወረቀ ካለው ግእዛዊ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ትርጉሙም እንትፍ አለ፣ (ተፋ) ማለት ነው፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ መጽሐፍ (ምዕራፍ ፶፥፮) “ፊቴንም ከውርደትና ከትፋት አልመለስኩም” ተብሎ እንደተነገረ እየዘበቱበት ምራቃቸውን ተፉበት (ማቴ. ፳፯፥፳፱-፴፤ ማር. ፲፭፥፲፱)፡፡ በኃጢአት የቆሸሸውን የሰውን ሕይወት ለማጥራት የመጣው ንጹሐ ባሕርይ አምላክ ተተፋበት፡፡ በሥራው ከገነት ተተፍቶ፤ ተንቆ፤ ተዋርዶ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ኃጢአትን ይቅር የሚል እርሱ ጌታችን ያለ ኃጢአቱ ተተፋበት፤ ተናቀ፤ ተዋረደ፡፡ እንኳን በአምላክ ፊት በሰው ፊት እንኳን መትፋት እጅግ ያስነውራል፡፡ እርሱ ግን የኃጢአታችንን ነውር ከእኛ ሊያጠፋ ነውር የሆነውን ምራቅ ተቀበለ፡፡
 
፬. ሰትየ ሐሞት (መራራ ሐሞት መጠጣት)

ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ሳለ ተጠማሁ ባለ ጊዜ መራራ ሐሞት መጠጣቱን የሚገልጥ ነው፡፡ “ሰተየ” ማለት ጠጣ ማለት ነው፡፡ ሐሞት የሚለውም አሞት ተብሎ በቁሙ ይተረጐማል፡፡ “ለመብሌ ሐሞት ሰጡኝ፣ ለጥማቴም ሆምጣጤ አጠጡኝ” (መዝ. ፷፰፥፳፩) ብሎ ነቢዩ ዳዊትን ትንቢት ያናገረ የነቢያት አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ “ተጠማሁ” ባለ ጊዜ ሆምጣጤ ተሞልቶበት ተቀምጦ ከነበረው ዕቃ ሆምጣጤውን በሰፍነግ ሞልተው ወደ አፉ አቀረቡለት፡፡ ውኃ አጠጡኝ ቢላቸው በሐሞት የተደባለቀ የወይን ጠጅ ሊጠጣ አቀረቡለት፡፡ ቀምሶም ሊጠጣው አልወደደም (ማቴ. ፳፯፥፴፬)፡፡ ጌታችንም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ “ተፈጸመ” አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ (ማቴ. ፳፯፥፵፰፤ ማር. ፲፭፥፴፮፤ ሉቃ. ፳፫፥፴፮፤ ዮሐ. ፲፱፥፳፱)፡፡


ቢጠጡት ለዘለዓለም የማያስጠማ ውኃ የሚሰጥ አምላክ፤ የተጠማችውን ነፍስ የሚያረካ ጌታ፤ ለዘለዓለም የሚፈልቅ የሕይወት ውኃ ምንጭ የሚያድል ፈጣሪ በተጠማ ጊዜ የፈጠረውን ውኃ እንኳን የሚያጠጣው የሚያቀምሰውም አላገኘም (ኢሳ. ፶፭፥፩)፡፡ አርባ ዓመት ሙሉ በቃዴስ በረሃ ሲጓዙ ለነበሩ አባቶቻቸው ከሰማይ መና አውርዶ የመገባቸው፤ ከአለት ላይ ውኃ አመንጭቶ ያጠጣቸው ክርስቶስ በተጠማ ጊዜ ቀዝቃዛ ውኃ ነፈጉት (ዘዳ. ፲፮፥፩-፳፤ ፩ቆሮ. ፲፥፫)፡፡ የዝናማት፤ የባሕርና የውቅያኖስ ጌታ በውኃ ጥም ተቃጠለ፡፡
 
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሲኦል በረሃ ወድቀው በሕይወት ውሃ ጥም የተቃጠሉትን ነፍሳት ለማርካት ሲል እርሱ ተጠማ፡፡ በኃጢአት ወድቀው፣ በበደል ረክሰው፣ በነፍሳቸው ተጐሳቁለው፣ መራራ መከራን የሚቀበሉትንና ምረረ ገሃነም አፉን ከፍቶ ሆዱን አስፍቶ የሚጠብቃቸውን ሁሉ ለማዳን መራራ ሐሞትን ቀመሰ፤ ሆምጣጣውንም ጠጣ፡፡ የመረረውን የሰው ልጆችን ሕይወት ለማጣፈጥ የመረረውን መጠጥ ተቀበለ፡፡

፭. ተቀሥፎ ዘባን (ጀርባውን መገረፍ)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጀርባው እስኪላጥ ያለ ርኅራኄ የመገረፉን ነገር የሚገልጥ ነው፡፡ “ተቀሥፎ” የሚለው ቃል ቀሠፈ- ገረፈ ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ “ዘባን” ደግሞ ጫንቃ፣ ትከሻ፣ ጀርባ ማለት ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጠው የተገረፈ አይሰቀልም፡፡ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም ነበር፡፡ ጲላጣስ ግን ኢየሱስ ክርስቶስን አስገረፈው፡፡ ከደሙ ንጹሕ ነኝ ብሎ ከታጠበ በኋላ ክርስቶስን ያለ ኃጢአቱ በመግረፍ ለአይሁድም አሳልፎ በመስጠት ‹‹ታጥቦ ጭቃ›› እንዲሉ የታጠበ እጁን መልሶ አቆሸሸው (ማቴ. ፳፯፥፳፰፤ ማር. ፲፭፥፲፭፤ ዮሐ. ፲፱፥፩)፡፡
 
መድኃኒታችን መንፀፈ ደይን ወድቆ በእግረ አጋንንት ተጠቅጥቆ በእሳት አለንጋ የሚገረፈውን የሰው ልጅ ለማዳን ሲል ጀርባውን ለግርፋት ሰጠ፡፡ ሥጋው አልቆ አጥንቱ እስኪቆጠር ተገረፈ፡፡ አይሁድ አገረ ገዥያቸው ጲላጣስ ላቀረበላቸው ምርጫ ይፈታላቸው ዘንድ ነፍሳትን ከሲኦል የሚያወጣውን ክርስቶስን ሳይሆን ራሱን እንኳን ከምድራዊ ወህኒ ማውጣት ያልቻለውን ወንበዴውን በርባንን መረጡ፡፡ መገረፍ ይገባው የነበረ በርባን ተለቀቀ፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ “ጀርባዬን ለገራፊዎች፣ ጉንጬንም ለጠጉር ነጪዎች ሰጠሁ” (ኢሳ. ፶፥፮) ተብሎ እንደተነገረ ጀርባውን ለገራፊዎች አሳልፎ ሰጠ፤ ጽሕሙንም ተነጨ፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው የሰው ልጅ ከሚያድነው አምላክ ይልቅ የሚገርፈውንና የሚዘርፈውን ወንበዴ መርጦ ስለተገኘ ነው፡፡
 
፮. ተዐርቆተ ልብስ (ከልብስ መራቆት)

አምላካችን ኢየሱስ ክርስስቶስ ልብሱን መራቆቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተዐርቆተ›› ማለት ታረዘ፤ ተራቆተ ማለት ነው፡፡ ፀሐይና ከዋክብትን ብርሃን አልብሶ የፈጠረ አምላክ ተራቆተ፡፡ ጸጋውን ለዕሩቃን የሚያለብስ አምላክ ልብሱን ተገፍፎ ዕራቁቱን ቆመ፡፡ ጨለማን ለብሶ ጨለማን ተንተርሶ ይኖር የነበረውን ሰው መልሶ ብርሃን ያለብሰው ዘንድ የብርሃናት ጌታ፣ የጸጋ ሁሉ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገፈፈ፤ ተራቆተ፡፡
 
የሲኦል ወታደሮች የሆኑት አጋንንት የሰውን ልጅ ጸጋ ገፍፈውት ነበርና ጲላጦስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አሳልፎ በሰጣቸው ሰዓት ወታደሮች ልብሱን ገፍፈውታል (ማቴ. ፳፯፥፳፯)፡፡ የሰው ልጅ ለቀረበለት ምርጫ የሰው ምላሽ ዘራፊው፤ ገራፊው ወንበዴ በርባን እንዲፈታለት ነበር፡፡ ‹‹አቅረብኩ ለከ እሳተ ወማየ፣ ደይ እዴከ ኅበ ዘፈቀድከ! እነሆ እሳትና ውኃን አቅርቤልሃለሁ፣ እጅህን ወደ ፈቀድከው ስደድ›› ሲባል የሰው ልጅ እጁን ወደ እሳት ሰደደ፡፡
 
፯. ርግዘተ ገቦ (ጎንን መወጋት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ጎኑን በስለታም ጦር መወጋቱን የሚገልጥ ነው፡፡ “ርግዘት” የሚለው ቃል ረገዘ- ወጋ ከተሰኘ የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ ገቦ ማለት ደግሞ ጎን ማለት ነው፡፡ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ አጠገብ፣ በግራና በቀኙ ሁለት ወንበዴዎች ተሰቅለው ነበር፡፡ ሥጋቸው በሰንበት በመስቀል ላይ እንዳይኖር ጭናቸው ተሰብሮ እንዲወርዱ አይሁድ ጲላጦስን በለመኑት መሠረት ጭፍሮቹ የሁለቱን ወንበዴዎች ጭን ጭናቸውን ከሰበሩ በኋላ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ሲመጡ ፈጽሞ እንደሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፡፡ ነገር ግን ከጭፍሮቹ አንዱ ጎኑን በጦር ስለወጋው ወዲያው ከጎኑ ደምና ውኃ ፈሰሰ፡፡(ዮሐ.፲፱፥፴፫)፡፡
 
አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ያደርገው ዘንድ ሞተ፤ የሰው ልጅ በዘለዓለማዊ ሞት ተይዞ ነበርና፡፡ ትልቁ ሞት በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር መለየት ነው፡፡ በጌታችን ሞት ግን ሞት ራሱ ድል ተነሣ፡፡ የሞት መውጊያ በሆነ ኃጢአት የሞተውን ሰው ለማዳን ጎኑን በጦር ተወጋ፡፡ በሰው ልቡና ተተክሎ የነበረውን ኃጢአት ከነሥሩ ነቅሎ ስለጣለው “ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ?” ተባለ፡፡ የሞት መውጊያው ኃጢአት ነበርና (፩ቆሮ. ፲፭፥፶፬-፶፭፤ ኢሳ. ፳፭፥፰፤ ሆሴ. ፲፫፥፲፬)


ከተወጋው የጌታችን ጎን ደምና ውኃ መፍሰሱም የእግዚአብሔርን ልጅነትና የዘለዓለምን ሕይወት አጥቶ የነበረው ሰው ልጅነቱና ሕይወቱ እንደተመለሰለት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ምክንያቱም ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ተጠምቆ ልጅነትን፣ ደሙንም ጠጥቶ የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛልና፡፡ (ዮሐ. ፫፥፭፤ ዮሐ. ፮፥፶፬)


 ፰. ተአሥሮተ ድኅሪት (ወደ ኋላ መታሠር)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት እጆቹን ወደኋላ የፊጥኝ መታሠሩን የሚገልጥ ነው፡፡ “ተአሥሮት” የሚለው ቃል አሠረ (ሲነበብ ይላላል) ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም አሠረ ማለት ነው፡፡ “ድኅሪት” የሚለው ቃል ደግሞ ተድኅረ- ወደኋላ አለ ከሚለው ግሥ የወጣ ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጊዜው በደረሰ ሰዓት ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ በሰጠባት በዚያች ዕለትና ሰዓት ሻለቃውና ጭፍሮቹ የአይሁድም ሎሌዎች እጁን የኋሊት አሥረው መሬት ለመሬት ጎትተውታል፡፡ አፍገምግመውታል (ዮሐ. ፲፰፥፲፪)፡፡
 
በኃጢአት ሰንሰለት የኋሊት ታሥሮ ጠላት ዲያብሎስ የሚያፍገመግመውን የሰው ልጅ ለማዳን፣ ሰውንም ከኃጢአት እሥራት ይፈታ ዘንድ ሲል መድኃኔዓለም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ የኋሊት ታሠረ፡፡
 
፱. አምሥቱ ቅንዋተ መስቀል

መድኃኒታችን በመስቀል ላይ የተቸነከረባቸውን ጠንካራ የብረት ችንካሮች (ምስማሮች) የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ቅንዋት›› የሚለው ቃል ቀነወ- ቸነከረ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ መስቀል ማለት ደግሞ ዝም ብሎ የቆመ ግንድ ሳይሆን አሁን በየሥፍራው እንደምናየው ምልክት የተመሳቀለ እንጨት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቸነከረባቸው አምስቱ ችንካሮች ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፤ ሮዳስ ይባላሉ፡፡ እነዚህም የአምሥቱ አዕማደ ምሥጢራት ምሳሌዎች መሆናቸውን አበው ያስተምራሉ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሰባቱ የመስቀል ላይ ጩኸቶች

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአይሁድ በይሁዳ አማካይነት ተላልፎ ከተሰጠበት ሐሙስ ምሽት ጀምሮ ስቃይ ሲያጸኑበት ቆይተዋል፡፡ በዕለተ ዐርብም ይሰቅሉት ዘንድ አስከ ቀራንዮ መስቀል አሸክመው የተለያዩ ጸዋትወ መከራ እያጸኑበት ወስደውታል፡፡ በመሰቀል ላይ በሁለቱ ወንበዴዎች መካከል ከተሰቀለበት ሰዓት ጀምሮም የተናገራቸው ቃላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን “ሰባቱ የመስቀል ላይ ጩኸቶች ወይም “ሰባቱ አጽርሐ መስቀል” በማለት ሰይማ ታስባቸዋለች፡፡ እነርሱም በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱ ሲሆን ቀጥለንም በዝርዝር እንመለከታቸዋለን፡-

፩ኛ. “ኤሎሄ ኤሎሄ ላማሰበቅታኒ፤ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ (ማቴ. ፳፯፥፵፮)

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሳለ በዘጠኝ ሰዓት የተናገረው ቃል እንደሆነ በወንጌል ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ “በዘጠኝ ሰዓትም ጌታችን ኢየሱስ ኤሎሄ ኤሌሄ ላማሰበቅታኒ ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸ፡፡ይኸውም አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ? ማለት ነው፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት በሰሙ ጊዜ ይህስ ኤልያስን ይጠራል አሉ” (ማቴ. ፳፯፥፵፯) እንዲል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ ብሎ የተናገረበት መሠረታዊ ሐሳብ፡- ያችን የድኅነት ቀን ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ያለችውን ዕለተ ዓርብ በተስፋ ይጠባበቅ የነበረውን አዳምን ወክሎ እንደሆነ አበው ያስረዳሉ፡፡ (ማቴ. ፳፯፥፵፭ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡ በመሆኑም አምላኬ አምላኬ ያለው በአዳም ተገብቶ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እንዲሁም አምላኬ አምላኬ ያለው ሰውነቱን ሲገልጥ ነው፡፡ ይህም ፍጹም አምላክነቱንና ፍጹም ሰውነቱን ማለት ነው፡፡

፪ኛ. “ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ (ሉ.፳፫፥፵፫)

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደል ሳይኖርበት እንደ በደለኛ ተቆጥሮ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ነበር የተሰቀለው፡፡ “ከእርሱ ጋር ሁለት ወንበዴዎችን አንዱን በቀኙ አንዱን በግራው ሰቀሉ፡፡ መጽሐፍ ከዐመፀኞች ጋር ተቈጠረ ያለው ተፈጸመ” (ማር. ፲፭፥፳፯) ይላልና፡፡

በቀኝ በኩል የተሰቀለው ወንበዴ ጌታችንን “አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ›” አለው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ እንዲህ አለው “እውነት እልሃለሁ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ፡፡” (ሉቃ. ፳፫፥፵፫)፡፡

፫ኛ. “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ (ሉቃ. ፳፫፥፵፮)

“ያን ጊዜም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድምጹን ከፍ አድርጎ አባት ሆይ ነፍሴን በአንተ እጅ አደራ እሰጣለሁ ብሎ ጮኸ፤ ይህንም ብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ሉቃ. ፳፫፥፵፮)፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” በማለት የተናገረው ቃል የተሰቀለው እርሱ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነና የአብ የባሕርይ ልጁ እንደሆነ ያሳያል፡፡

፬ኛ. “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው (ሉቃ. ፳፫፥፴፬)

ምንም በደል ሳይኖርበት አይሁድ በክፋት ተነሳስተው መከራ አጸኑበት፤ ያን ሁሉ የግፍ ግፍ በጭካኔ የተሞላ መከራ ሲያደርሱበት ልባቸውን ዲያብሎስ ስላደነዘዘው የሚራራ ልብ አጡ፡፡በዚያንም ጊዜ መምህረ ይቅርታ ቸሩ አምላካችን ለሠቃዮቹ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው አለ” (ሉቃ. ፳፫፥፴፬)፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደለኞች ይቅርታን ያገኙ ዘንድ ይቅር በላቸው አለ፡፡ ልመናውንም ያቀረበው ወደ ባሕርይ አባቱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ጋር ደግሞ በባሕርይ፣ በሕልውና፣ በአገዛዝ፣ በፈቃድ አንድ ናቸው፡፡ እንዲሁም የሰውን ባሕርይ ባሕርይ አድርጎ ፍጹም ሰው እንደሆነ ሲያስረዳ ነው፡፡ ይህም በደለኞችን ከራሱ ጋር ያስታረቀበት የፍቅር ድምጽ ነው፡፡

አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅርበላቸው ማለቱ አባት ሆይ ብሎ የባሕርይ ልጅነቱን ከመግለጹ በተጨማሪ ይቅር በላቸው ማለቱ ጠላትን ይቅር ማለት የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ የመሆኑ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ምክንያቱም ጠላቶቻችሁን ውደዱ ብሎ ያስተማረ እርሱ ብቻ ነውና፡፡

፭ኛ. “እነሆ ልጅሽ፤ እናትህ እነኋት (ዮሐ. ፲፱፥፳፮)

“ጌታችን መድኀኒታችንን ኢየሱስም እናቱንና የሚወደውን ደቀ መዝሙሩን ቆመው ባያቸው ጊዜ እናቱን ‘አንቺ ሆይ እነሆ ልጅሽ’ አላት፡፡ ከዚህም በኋላ ደቀ መዝሙሩን ‘እናትህ እነኋት’ አለው፡፡ ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ተቀብሎ ወደ ቤቱ ወሰዳት” (ዮሐ. ፲፱፥፳፮)፡፡ ደቀ መዝሙሩ ተብሎ የተጠቀሰው ጌታችን ይወደው የነበረ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊው ነው፡፡ ይህንንም የጻፈው እርሱ ነው (ዮሐ. ፳፩፥፳፬)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ከዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት አንዱ ቢሆንም ሐሙስ ማታ እረኛው ሲያዝ ከተበተኑት በጎች ጋር አብሮ አልሸሸም፡፡ በዚያች በአስጨናቂዋ ሰዓት ከጌታችን ጋር እስከ እግረ መስቀሉ ተጓዘ፡፡የክርስቶስ ፍቅር ፍርሃቱን ሁሉ አርቆለት የአይሁድን ቁጣና ዛቻ ሳይፈራ ጸንቶ በመቆሙ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለእኛ ሁሉ እርሱ በኩል ተሰጠችን፡፡ እናታችን ድንግል ቅድስት ማርያም ሁል ጊዜም ቢሆን ከእግረ መስቀሉ ሥር ለሚገኙ፣ ልባቸው ቀራንዮን ለሚያስብ ሁሉ እናት እንድትሆን እነርሱም ልጆቿ እንዲሆኑ በቅዱስ ዮሐንስ በኩል ተሰጥታናለች፡፡

በመሆኑም “እነሆ ልጅሽ፤ እናትህ እነኋት” የሚለው የመስቀሉ ቃል በመስቀል ላይ የተከፈለልንን ዋጋ አስበን በእርሱ አምነን በምግባር ታንጸን እንደ ፈቃዱ በምንኖር ክርስቲያኖችና ለድኅነታችን ምክንያት በሆነች በእመ አምላክ በቅድስት ድንግል ማርያም መካከል የእርሷ እናትነት፣ የእኛ ልጅነት የተመሠረተበት የፍቅር ቃል ነው፡፡

፮ኛ. “ተጠማሁ (ዮሐ. ፲፱፥፳፰)

“ከዚህም በኋላ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ሁሉ እንደ ተፈጸመ ባየ ጊዜ የመጽሐፍ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‘ተጠማሁ’ አለ” (ዮሐ. ፲፱፥፳፰)፡፡

ውኆችን በእፍኙ የሰፈረ፣ የባሕር አሸዋን የቆጠረ፣ ውኆችንም ጠርቶ በምድር ፊት ላይ የሚያፈሳቸው፣ የባሕር ጥልቀትንና ዳርቻን የወሰነ፣ የኤርትራን ባሕር እንደ ግድግዳ ያቆመ አምላክ “ተጠማሁ” ብሎ ጮኸ፡፡ (ኢሳ. ፵፥፲፪፣አሞ. ፱፥፮)፡፡

“የተጠማ ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ በእኔም የሚያምን መጽሐፍ እንደ ተናገረ የሕይወት ውኃ ምንጭ ከሆዱ ይፈልቃል” (ዮሐ. ፯፥፴፯) በማለት እርሱ የሕይወት ውኃ እንደሆነ ተናገረ፡፡ አምላክ ሲሆን “ተጠማሁ” ብሎ መጮኹ ስለ ምንድንነው ብለን ቅዱሳት መጻሕፍትን ስንመረምር፡- አንደኛ የመከራውን ጽናት፣ ከሚነገረው በላይ መከራውን እንዳጸኑበት የሚያሳይ ሲሆን፤ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ እርሱ የተጠማው የሰውን መዳን ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በዚያን ወቅት እንኳ ከክፉ ሥራው ተመልሶ የሚጸጸት፣ የሚራራ፣ ንስሓ የሚገባ ሰው በማጣቱ መድኃኒት እርሱ ቀርቦ ሳለ የሰው ልጅ ባለማስተዋሉ ወደ እርሱም በፍቅር ባለመቅረቡና ባለመመለሱ ተጠማሁ አለ፡፡

፯ኛ. “ሁሉ ተፈጸመ (ዮሐ. ፲፱፥፴)

”ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስም ሆምጣጤውን ቀምሶ ሁሉ ተፈጸመ አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ዮሐ.፲፱፥፴)፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕተ ዐርብ በመስቀል ላይ ሳለ ‘ተፈጸመ’ ብሎ መናገሩ ብዙ ትርጉም ያለው ቃል ነው፡፡

በነቢያት ስለ እኔ የተነገረው ትንቢት፣ የተመሰለው ምሳሌ፣ በቅዱሳን አበው የተቆጠረው ሱባኤ፣ ጊዜው ደርሶ የአዳም ተስፋ ተፈጸመ፡፡

የሰው ልጅ በዲያብሎስ አገዛዝ በሞትና በጨለማው ሥልጣን፣ በአጋንንት ወጥመድ ታስሮ የሚኖርበት የፍዳ ዘመን አለቀ ተፈጸመ፡፡

በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰማይና በምድር መካከል ቆሞ የነበረው የጥል ግድግዳ ፈረሰ፣ የተጻፈው የዕዳ ጽሕፈት ተደመሰሰ፣ የሰው ልጅ ዕዳ በደል ተከፈለ በአምላክ የቤዛነት ሥራ ሁሉ ተፈጸመ ማለት ነው፡፡

እነዚህ ከአንድ እስከ ሰባት የጠቀስናቸው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መራራውን መከራ እየተቀበለ የተናገራቸው የመጨረሻ ቃላቶቹ ናቸው፡፡ ወደዚህ ዓለም ሰው ሆኖ የመጣበትን ዓላማ አከናውኖ ሲጨርስ በመጨረሻ “ተፈጸመ ኵሉ” በማለት ነፍሱን ከሥጋው ለየ፡፡ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶም በሲኦል ባርነት ለነበሩት አዳምና ልጆቹ ነጻነትን ሰበከላቸው፡፡ በአካለ ሥጋ ደግሞ ወደ መቃብር ወርዶ ሙስና መቃብርን አጠፋልን፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን፡፡

ጸሎተሐሙስ

በሰሙነ ሕማማት ባሉት ከሰኞ እስከ ረቡዕ ያሉትን ቀናት በተመለከተ በተከታታይ ስናቀርብ ቆይተናል፡፡ ዕለተ ሐሙስ የተለያዩ ስያሜዎች ያሉት ሲሆን ጥቂቶቹን ቀጥለን እናቀርባለን፡፡

. ጸሎተ ሐሙስ፡- በዚህች ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አይሁድ መጥተው እስከሚይዙት ድረስ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል ጴጥሮስን፣ ዮሐንስንና ያዕቆብን ይዞ የአትክልት ቦታ በሆነው በጌቴሴማኒ ጸልዮአል፡፡ “ጴጥሮስንና ሁለቱን የዘብዴዎስ ልጆችን (ዮሐንስንና ያዕቆብን) ልጆች ወሰደ፡፡ ያዝንና ይተክዝ ጀመር፡፡ ከዚህም በኋላ ‘ነፍሴ እስከ ሞት ድረስ እጅግ አዘነች፤ በዚህ ተቀመጡ፤ ከእኔም ጋር ትጉ” አላቸው፡፡ ከዚህም ጥቂት ፈቀቅ አለና በግንባሩ ሰግዶ ጸለየ” (ማቴ. ፳፮፥፴፮-፵፮) በዚህም ምክንያት የጸሎተ ሐሙስ ቀን ተብሏል፡፡

ከዚህም በኋላ እርሱ ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ ጋር ስላለው አንድነትና ክብር ለሐዋርያት ካስተማራቸው በኋላ የአስቆሮቱ ይሁዳ ይህችን ሥፍራ ቀድሞ ጌታ ይወዳት እንደነበር ያውቃልና የካህናት አለቆችንና ጸሐፍት ፈሪሳውያንን እንደዚሁም ጋሻና ጦርም የያዙትን ጭፍሮች አስከትሎ ወደ እርሱ መጣ፡፡ በዚህም ጊዜ ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን ተነሡ እንሒድ! እነሆ አሳልፎ የሚሰጠኝ ቀርቧል አላቸው፡፡ ወደ ካህናት አለቆችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን ቀርቦም ማንን ትሻላችሁ? አላቸው፤ እነርሱም “የናዝሬቱን ኢየሱስን አሉት፡፡ (ዮሐ. ፲፰፥፩-፯) ያንጊዜም ይሁዳ ወደ እርሱ ቀርቦ፤ መምህር ሆይ ቸር አለህን፤ ሰላም ላንተ ይሁን›› ብሎ ሳመው፤ መሳሙም ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል የትኛው እንደሆነ ለአይሁድ ለይቶ ለማሳየት የተጠቀመው የጥቆማ ምልክት ነበር፡፡ ምክንያቱም የጌታ መልክና የወንጌላዊው የዮሐንስ መልክ ይመሳሰልባቸው ነበርና ለይቶ ሲያሳያቸው ነው፤ ያንጊዜም ጌታችን የሰውን ልጅ በመሳም አሳልፈህ ትሰጠዋለህን? ብሎታል፡፡ (ሉቃ. ፳፪፥፵፰)

ከዚህም በኋላ አይሁድና ጭፍሮቻቸው ጌታ ኢየሱስን በስድስተኛው ሰዓተ ሌሊት ያዙት፡፡ ወደ ሽማግሌዎችና ወደ ሊቀ ካህናቱ ወደ ቀያፋ ወሰዱት፡፡

. የምሥጢር ቀን፡ ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን መካከል አንዱ የሆነው ምሥጢረ ቊርባን የተመሠረተው በዚች ዕለት ነውና ይህቺ ዕለት የምሥጢር ቀን ተብላ ትጠራለች፡፡

መድኃኒታችን ክርስቶስ በዚህች ዕለት ሐሙስ ለዓርብ ምሽት በሁለተኛው ሰዓተ ሌሊት

ኅብስቱን ባርኮ ለዐሥራ ሦስት ከፈተተ በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ ሰጥቶአቸዋል፡፡ “ጌታችን ኢየሱሰስ ኅብስቱን አንሥቶ ባረከ፣ ቈረሰ፣ ለደቀ መዛሙርቱም “ይህ ሥጋዬ ነው፤ እንኩ ብሉ፤ ብሎ ሰጠ፡፡ ጽዋውንም አንሥቶ አመስግኖ ሰጣቸው፤ እንዲህም አለ፡- ሁላችሁም ከእርሱ ጠጡ፡፡ ኃጢአትን ለማስተስረይ ስለ ብዙዎች የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው” አላቸው

ዐሥራ ሦስተኛውን ደግሞ ምንም የሚጠቅመው ባይሆንም ለእርሱ የሚቀበለው አድርጎታል፡፡ ቀምሶ አቀመሳቸው እንዲል፡፡ አንድም አብነት ለመሆን እንደዚሁም ነገ በመልዕልተ መስቀል ዐሥራ ሦስቱን ሕማማተ መስቀል እቀበላለሁ ሲል ነው፡፡ ጌታ ይህን አርአያነት ባያደርግልን ኖሮ ዛሬ ካህኑ የጌታን ሥጋና ደም ሳይቀበል አቀብሎ ብቻ በሄደ ነበርና ይህን ሥርዓት ለማስተማር ነው፡፡ (አንድምታ ቅዳሴ ማርያም)

በዚህም መሠረት እኛ ከእርሱ ከመድኃኒታችን ክርስቶስ ጋር፣ አንድ የምንሆንበትን ምሥጢር ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠባት ዕለት በመሆንዋ ይህቺ ዕለት የምሥጢር ቀን ተብላ ትጠራለች፡፡በዚች ዕለት የቅዳሴ አገልግሎት የሚፈጸም ሲሆን የቅዳሴው ሥርዓትም ዝቅ ባለ ድምጽ በለሆሳስ ነው፡፡ የቃጭሉን አገልግሎት የሚተካው ጸናጽል ሲሆን ይህም አይሁድ ጌታችንን ሊይዙት በመጡ ጊዜ ድምጻቸውን ዝግ አድርገው በለሆሳስ እየተነጋገሩ መምጣታቸውን ለማሰብ ነው፤ በቅዳሴውም ጸሎተ ተአምኆ፣ ሥርዓተ ኑዛዜ የማይደረግ ሲሆን ሥርዓተ ቊርባን ግን ይፈጸምበታል፡፡ ይህም የሚደረገው ጌታችን ለእኛ ለምእመናን የሰጠውን ዘለዓለማዊ ቃል ኪዳን ለማሰብ ነው፡፡ በዚችም ዕለት ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን ቀድመው ራሳቸውን በንስሓ በማዘጋጀት ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ይቀበሉባታል፡፡

. የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ፡ ይህቺ ዕለት መድኃኒት ክርስቶስ ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጐ የገለጠባት በእንስሳት ደም ይቀርብ የነበረው መሥዋዕተ ኦሪትም አብቅቶ አማናዊው የሐዲስ ኪዳን መሥዋዕት ለድኅነተ ዓለም የተበሠረባትና የተጀመረባት ዕለት በመሆንዋ የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ እየተባለች ትጠራለች፡፡ መድኃኒት ክርስቶስ ይህ ጽዋዕ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን ሐዲስ ኪዳን ነው፡፡ ከእርሱም ጠጡ በማለት እንደተናገረው፡፡ (ሉቃ. ፳፪፥፳)

. የሕፅበተ እግር ቀን፡ በዚህች ዕለት በመጀመሪያው ሰዓተ ሌሊት በመጽሐፍ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፤ በኋላም በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበት ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ። ወደ ስምዖን ጴጥሮስም መጣ እርሱም፦ጌታ ሆይ፥ አንተ የእኔን እግር ታጥባለህን? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፥ በኋላ ግን ታስተውላለህ አለው። ጴጥሮስም የእኔን እግር ለዘለዓለም አታጥበኝም አለው። ኢየሱስም ካላጠብሁህ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም ብሎ መለሰለት። ስምዖን ጴጥሮስም ጌታ ሆይ እጄንና ራሴን ደግሞ እንጂ እግሬን ብቻ አይደለም አለው። ኢየሱስም፦ የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፥ ሁለንተናው ግን ንጹሕ ነው፤ እናንተም ንጹሓን ናችሁ፤ ነገር ግን ሁላችሁም አይደላችሁም አለው። አሳልፎ የሚሰጠውን ያውቅ ነበርና፡፡ ስለዚህ ሁላችሁ ንጹሓን አይደላችሁም አለ። እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ ተቀመጠ፥ እንዲህም አላቸው፦ያደረግሁላችሁን አስተውላችኋልን? እናንተ መምህርና ጌታ ትሉኛላችሁ፤ እንዲሁ ነኝና መልካም ትላላችሁ። እንግዲህ እኔ መምህርና ጌታ ስሆን እግራችሁን ካጠብሁ፥ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ እግራችሁን ትተጣጠቡ ዘንድ ይገባችኋል። እኔ ለእናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና ተብሎ በወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደ ተጻፈ፡፡ (ዮሐ. ፲፫፥፬-፲፭)

እንግዲህ ከዚህ በላይ ከተጠቀሰው ከወንጌላዊው ቃል እንደምንረዳው ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር ያጥብ ዘንድ በጴጥሮስ ጀምሮአል፡፡ ጴጥሮስ ግን እኔ የአንተ ደቀ መዝሙር ስሆን ባንተ በመምህሬ ልታጠብ አይገባኝም አለ፤ ጌታችንም መልሶ እውነት እውነት እልሃለሁ፤ እኔ እግርህን ካላጠብኩህ ከእኔ ጋር ዕድል ፈንታ የለህም፡፡ ከዚህም በኋላ ሌሎቹንም ሐዋርያት አጥቦአቸዋል፡፡ አሳልፎ የሚሰጠውን ይሁዳን እንኳን ሳይቀር እግሩን አጥቦታል፡፡ ጌታም ይህንን ያደረገው አሳልፎ እንደሚሰጠው ሳያውቅ ቀርቶ አልነበረም፤ ፍቅርን ሲያስተምረው ለንስሓም ጊዜን ሲሰጠው እንጂ፤ በሌላ በኩል ደግሞ እኛንም ለሚወዱን ብቻ ሳይሆን ለሚጠሉን እንኳን በጎ ማድረግ እንደሚገባን ሲያስተምረን ነው፡፡ (ዮሐ. ፲፫፥፰)

በዚህም መሠረት ይህንን ሥርዓቱን አብነት በማድረግ በዚች ቀን ዘጠኝ ሰዓት ሲሆን የሕፅበተ እግር ሥርዓቱ በሚከናወንበት ጊዜ ዲያቆኑ ውኃን ያቀርባል፤ በቀረበውም ውኃ ላይ ጸሎተ አኰቴት ይጸለያል፡፡ ወንጌል ተነብቦ ውኃው በካህኑ ወይም በሊቀ ጳጳሱ እጅ ይባረክና የሕጽበተ እግር ሥርዓቱ ከካህናት እስከ አናጕንስጢስ እንደዚሁም ከወንዶች እስከ ሴቶች ላሉት ምእመናን ሁሉ በካህናቱ እጅ ይከናወናል፡፡

በዚህም ጊዜ ከውኃው በተጨማሪ የወይራና የወይን ቅጠልንም ለሥርዓቱ ማስፈጸሚያነት እንጠቀምባቸዋለን፤ ምሥጢሩም ወይራ ጽኑዕ ነው፡፡ ይህም ክርስቶስ ጽኑ መከራ መቀበሉን የሚያስረዳ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም እኛም የእርሱን መከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ነው፡፡ የወይኑ ቅጠል ደግሞ በወይን የተመሰለ ደሙን አፍስሶ ለምእመናን የሕይወት መጠጥ ይሆናቸው ዘንድ መስጠቱን ለማዘከር ሲሆን በዚች ዕለት ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብ የፈጸመው የኅጽበተ እግር ሥርዓትም ለካህናትና ለምእመናን የትሕትና ሥራን ለማስረዳት መሆኑን እናንተም ለባልንጀሮቻችሁ እንዲሁ አድርጉ በማለት ነግሮናል፡፡

 የሕጽበተ እግር ሥርዓት ከተጠናቀቀ በኋላ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖ ምእመናን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ (ማቴ. ፳፮፥፳፮ ፥ ዮሐ. ፲፫፥፲)

ሰሙነ ሕማማት ዕለተ ረቡዕ

በሰሙነ ሕማማት ሰኞ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መራቡንና ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን በለስ አግኝቶ ፍሬ አልባ ቅጠል ብቻ ሆና አግኝቷታልና “እንግዲህ ወዲህ ለዘለዓለም ፍሬ አይኑርብሽ” በማለት እንደ ረገማትና ወዲያውኑ በለሲቱ እንደ ደረቀች የሚታሰብበት ቀን እንደሆነ ባለፉት ክፍሎች ተመልክተናል፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፲፰-፲፱) 

በሰሙነ ሕማማት ዕለተ ማክሰኞ (ሁለተኛ ቀን) ደግሞ የጥያቄ ቀን በመባል እንደሚታወቅ ተገልጿል፡፡ ሹመትን ወይም ሥልጣንን ለሰው ልጅ የሰጠ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰኞ ዕለት አንጽሖተ ቤተ መቅደስን ከፈጸመ በኋላ በዕለተ ሠሉስ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ ሲያስተምር የካህናት አለቆችና የሕዝቡ ሽማግሌዎች ወደ እርሱ መጥተው “በማን ሥልጣን ይህ ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ?” በማለት ጠይቀውታልና የጥያቄ ቀን በመባል ይታወቃል፡፡ እንዲሁም ዕለተ ሠሉስ የትምህርት ቀን በመባልም ይጠራል፡፡ ጌታችን ከፍቅረ እግዚአብሔር የተለዩትን አስተምሮ ማቅረብና መክሮ መመለስ እንደሚገባን በቤተ መቅደስ ውስጥ ሆኖ ረጅም ትምህርት በማስተማሩ የተሰጠው ስያሜ ነው፡፡

በዕለተ ረቡዕ የሚከተሉት ሦስት ነገሮች ተፈጽመዋል፡-

ምክረ አይሁድ፡- የካህናት አለቆች፣ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ ተማክረዋል፡፡ “ፋሲካም የሚባለው የቂጣ በዓል ቀረበ፡፡ የካህናት አለቆችና ጻፎችም ሊገድሉት ይሹ ነበር፤ ነገር ግን ሕዝቡን ይፈሩአቸው ነበር፡፡ ቁጥሩ ከዐሥራ ሁለቱ በነበረው በስቆርቱ ይሁዳ ልብ ሰይጣን አደረ፡፡ ሄዶም ከካህናት አለቆችና ከታላላቆች ጋር እርሱን አሳልፎ እንዲሰጣቸው ተነጋገረ” እንዲል፡፡ (ሉቃ. ፳፪፥፩)

በዚህም መሠረት ይህቺ ዕለት የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ፈሪሳውያን ጌታ ኢየሱስን እንዴት መያዝ እንዳለባቸው ምክር የመከሩበት፣ ምክራቸውንም ያጸኑበትና ሰቅለው ይገድሉት ዘንድ የወሰኑበት ቀን በመሆኑ የአይሁድ የምክር ቀን ተብላ ትጠራለች፡፡ በዚሁ ምክራቸው ወቅት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን  እንዴት አድርገው እንደሚይዙት በጣም ይጨነቁ ነበር፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ወቅቱ የፋሲካ በዓላቸውን የሚያከብሩበት ወቅት በመሆኑ በጌታችን ትምህርት የተማረኩ ብዙ ሕዝብ ትምህርቱን ያደንቁ ስለነበር ሁከት እንዳይፈጠር ከመፍራታቸው የተነሣ ነው፡፡ በዚህ ጭንቀት ሳሉ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል አንዱ የሆነው የአስቆሮቱ ይሁዳ በመካከላቸው ተገኝቶ ጌታችንን በመሳም አሳልፎ እንደሚሰጣቸው ለዚህ ተግባሩም ሠላሳ ብር ወረታውን እንዲከፍሉት ከእነርሱ ጋር በመስማማቱና የምክራቸው ተባባሪ በመሆኑ ጭንቀታቸውን አስወግዶላቸዋል፡፡ (ማር. ፲፬፥፲)

የመልካም መዓዛ ቀን፡- ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ ራስዋን በዝሙት አስገዝታ ትኖር የነበረችው ማርያም እንተ ዕፍረት (ባለ ሽቱዋ ማርያም) ሽቱ ቀብታዋለች፡፡ “እርሱም በቢታንያ በለምጻሙ በስምዖን ቤት በማዕድ ተቀምጦ ሳለ አንዲት ሴት ዋጋው የከበረ ጥሩ የናርዶስ ሽቱ የሞላበት የአልባስጥሮስ ብልቃጥ ይዛ መጣች፤ ብልቃጡንም ከፍታ በራሱ ላይ አፈሰሰችው” (ማር. ፲፬፥፫) በዚህም ምክንያት ዕለቱ የመልካም መዓዛ ቀን ተብሏል፡፡

የዕንባ ቀን፡ ማርያም እንተ ዕፍረት በጌታችን እግር ላይ ተደፍታ መላ ኃጢአቷን ይቅር እንዲላት በዕንባዋ እግሩን እያጠበች በፀጉሯም እግሩን እያበሰች ስለ ኃጢአቷ ሥርየት ተማጽናዋለችና የዕንባ ቀን በመባልም ተሰይሟል፡፡ (ማቴ.፳፮፥፮-፲፫፣ ማር.፲፬፥፫-፱፣ዮሐ.፲፪፥፩-፰)

የሰሙነ ሕማማት ሁለተኛ ቀን

ከሰሙነ ሕማማት ዕለታት ውስጥ ዕለተ ሠሉስ የጥያቄ ቀን በመባል ይታወቃል፤ ምክንያቱም ሹመትን ወይም ሥልጣንን ለሰው ልጅ የሰጠ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰኞ ዕለት አንጽሖተ ቤተ መቅደስን ከፈጸመ በኋላ በዚህች ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ ሲያስተምር የካህናት አለቆችና የሕዝቡ ሽማግሌዎች ወደ እርሱ መጥተው “በማን ሥልጣን ይህ ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ?” በማለት ጠይቀውታል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ እኔም አንዲት ቃል እጠይቃችኋለሁ፣ የነገራችሁኝ እንደሆነ እኔም በምን ሥልጣን ይህን እንደማደርግ እነግራችኋለሁ” አላቸው፡፡ ጌታችንም ጥያቄውን ይመልሱለት ዘንድ “የዮሐንስ ጥምቀቱ ከየት ነው? ከሰማይ ነውን? ወይስ ከሰው?ሲል ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም እርስ በርሳቸው ተነጋግረው እንዲህ አሉ “ከሰማይ ነው ብንለው እንኪያ ለምን አላመናችሁትም? ይለናል፡፡ ከሰው ነው ብንለውም ዮሐንስን ሁሉም እንደ ነቢይ ያዩታልና ሕዝቡን እንፈራቸዋለን ተባባሉ፡፡ በመጨረሻም መልስ መስጠት ስላልቻሉ “ከወዴት እንደሆነ አናውቅም” ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም “እንኪያስ እኔም በምን ሥልጣን ይህን እንደማደርግ አልነግራችሁም” አላቸው፡፡

ይህን ጥያቄ መጠየቃቸውም እርሱ የሚያደርጋቸውን ተግባራት ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተውት አልነበረም፤ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ ነበር እንጂ፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፳፫-፳፯ ፤ ማር. ፲፩፥፳፯-፴፫፣ ሉቃ. ፳፥፩-፰) በዚህም ምክንያት የሰሙነ ሕማማት ማክሰኞ የጥያቄ ቀን ይባላል፡፡

ዕለተ ሠሉስ ዕለተ ትምህርት ወይም የትምህርት ቀን በመባልም ትጠራለች፡፡ ጌታችን በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት በማስተማሩ የተሰጠው ስያሜ ሲሆን ይኸውም ከሃይማኖት የራቁትን፣ ከፍቅረ እግዚአብሔር የተለዩትን አስተምሮ ማቅረብና መክሮ መመለስ እንደሚገባን ሲገልጽልን ነው፡፡

በዚህም ትምህርቱ ሁለት ወንድማማቾችን አባታቸው ወደ ወይን ቦታ ሄደው ይሠሩ ዘንድ እንደጠየቃቸው፤ የመጀመሪያው እምቢ ቢልም ተጸጽቶ ሊሠራ መሄዱን፤ ሁለተኛውም እሺ ብሎ ነገር ግን ቃሉን አጥፎ ሳይሄድ መቅረቱን ነገራቸው፡፡ እርሱም ትምህርቱን ከነገራቸው በኋላ አስተምሮ ብቻ አልተዋቸውም፤ ጥያቄውን አስከትሏል፡፡ “እንግዲህ ከሁለቱ የአባቱን ፈቃድ የፈጸመ ማንኛው ነው?” ሲል ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም “ፊተኛው ነዋ” አሉት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ ሲል ገሠጻቸው፡- “እውነት እላችኋለሁ፤ ቀራጮችና አመንዝሮች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሟችኋል፡፡ ዮሐንስ ወደ እናንተ በጽድቅ ጎዳና መጣ፤ አላመናችሁበትም፣ ቀራጮችና አመንዝሮች ግን አመኑበት፤ እናንተም በኋላ በእርሱ ለማመን አይታችሁ እንኳ ንስሓ አልገባችሁም” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፳፰ ፤ ፳፭፥፵፮ ፤ ማር. ፲፪፥፪ ፤ ፲፫፥፴፯ ፤ ሉቃ. ፳፥፱ ፤ ፳፩፥፴፰)

ሌላው በዚሁ ቀን በምሳሌ ያስተማረው ትምህርት ስለ ወይን እና ወይኑን የተከለው ባለቤት ድካም የተመለከተ ነበር፡፡ “ሌላ ምሳሌ ስሙ፤ ባለቤት ሰው ወይንን ተከለ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፤ መጭመቂያም አስቆፈረለት፤ ግንብንም ሠራለት፤ ለገባሮችም ሰጥቷቸው ሄደ፡፡ የሚያፈራበት ወራት በደረስ ጊዜም ከወይኑ ፍሬ ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮቹን ወደ ገባሮቹ ላከ፡፡ ገባሮቹም አገልጋዮቹን ይዘው አንዱን በበትር ደበደቡት፣ አንዱንም ገደሉት፣ ሌላውንም በድንጋይ መቱት፡፡” በማለት አስረዳቸው፡፡ በዚህም ብቻ አላበቃም ሌሎችን ከዚህ በፊት ከላካቸው አገልጋዮች ቁጥር በላይ ወደ ገባሮቹ ሰደዳቸው፡፡ ነገር ግን ገባሮቹ የተላኩትን አገልጋዮች ደብድበው አባረሯቸው፡፡

ባለ ወይኑ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ ልጄን ያከብሩትና ይፈሩት ይሆናል ብሎ አንድ ልጁን ከወይኑ ያመጣለት ዘንድ ወደ ገባሮቹ ላከው፡፡ ገባሮቹም ልጁን ባዩት ጊዜ እርስ በርሳቸው “እነሆ ወራሹ ይህ ነው፤ ኑ እንግደለውና ርስቱን እንውረስ ተባባሉ፡፡ ይዘውም ከወይኑ ቦታ ውጭ አውጥተው ገደሉት፡፡ እንግዲህ የወይኑ ቦታ ባለቤት በመጣ ጊዜ እነዚህ ገባሮች ምን ያደርጋቸዋል?” ሲል ጠየቃቸው፡፡

የካህናት አለቆችንና የሕዝቡ ሽማግሌዎችም “ክፉዎችን በክፉ ያጠፋቸዋል፤ ወይኑንም በየጊዜው ፍሬውን ለሚሰጡት ለሌሎች ገባሮች ይሰጣል” አሉት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ አላቸው”… ግንበኞች የናቁአት ድንጋይ የማዕዘን ራስ ሆነች፡፡ … ስለዚህ እላችኋለሁ፡- የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ ትወሰዳለች፤ ፍሬዋንም ለሚያደርጉ ለአሕዘብ ትሰጣለች፡፡ በዚያችም ድንጋይ ላይ የሚወድቅ ይቀጠቀጣል፡፡፣ በላዩ የሚወድቅበትንም ትፈጨዋለች” የካህናት አለቆችና ጸሐፍት ፈሪሳውያንም ይህ ስለ እነርሱ የተነገረ መሆኑን ዐወቁ፡፡ (ማቴ.፳፩፥፴፫-፵፮)

ለሦስተኛ ጊዜም ለልጁ ሠርግ ስለ አደረገው ንጉሥ በምሳሌ አስተማራቸው፡፡ እነርሱ ግን ያስተማራቸውን ትምህርት ተረድተው ወደ ንስሓ ከመመለስ ይልቅ ጌታችን መድኃነኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስን በአነጋገሩ ያጠምዱትና ይይዙት ዘንድ ተማከሩ፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፳፫-፵፭ ፤ ፳፪፥፩-፳፪)፡፡

ይቆየን

“ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አድርጉ።” (ማቴ. ፫፥፰)

በደሳለኝ ብርሃኑ

ክፍል ሁለት

የንስሓ እንቅፋቶች

፩. ኃጢአትንና ጽድቅን ለይቶ አለማወቅ:- ድንቁርና ጨለማ ነው። ኃጢአት በውኃ ይመሰላል፣ ውኃ የተኛበት መሬት ከስር ምን እንዳለ እንደማይታወቅ የኃጢአት ውኃ የተኛበትም ሰው ኃጢአቱ ከእርሱ እስኪወገድ ድረስ ምንም አያውቅም። ኃጢአት ልብን ይደፍናል። “ሕዝቤ ዕውቀት ከማጣት የተነሣ ጠፋ” (ሆሴ. ፬) እንዳለው ነቢዩ ኃጢአትና ጽድቅን ለይቶ አለማወቅ የንስሓን በር ይዘጋብናል። ቅዱስ ጳውሎስ ከመመለሱ በፊት መልካም የሠራ እየመሰለው ከአይሁድ ጋር ክርስቲያኖችን ያሳድድ ነበር፣ በኋላ ግን ይህንን የልጅነትን(የአላዋቂነትን) ጠባይ ሽሯል። እግዚአብሔር አንድ የመዳኛ መንገድ ይፈልጋል፣ ምክንያት ፈልጎ ያድናል። ሰው ስለተማረ ብቻ ጽድቅን መሥራት አይችልም፤ በተጨማሪም ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ያስፈልጋል። ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደተናገረው “ክርስቲያን ክርስቲያን ካልሆኑት ሰዎች የሚለየው የሚጠቅመውን እና የማይጠቅመውን ለይቶ ማወቁ ነው፡፡” በኃጢአት ውስጥ ያለ ሰው እንደታመመ፣ ኃጢአት እየሠራ መሆኑን ሊያውቀው ይገባል።

፪. ለራስ ይቅርታ ማድረግ:- ሰው ራሱን መካድ አለበት እንጂ ለራሱ ይቅርታ ማድረግ የለበትም። “እኔን ሊከተል የሚወድ ራሱን ይካድ” (ማቴ. ፲፮፥፳፬። ከእኛ በላይ ለራሳችን የሚያዝነው እግዚአብሔር ነው እንጂ እኛ ለራሳችን ልናዝን አይገባም። ለራስ ይቅርታ ማድረግ ከቀድሞ አሁን ተሻሽያለሁ ማለትና ራስን ማጽደቅ ነው። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “ጥቂት እንደበደልክ አትንገረኝ። የኃጢአት ጠባዩ አንድ ነው፣ ልዩነት የለበትም” ይላል። ሰይጣን በዕድሜ፣ በኑሮ ሁኔታ፣ በጓደኛ እና በመሳሰሉት እያሳበበ ኃጢአት ያሠራናል። በኋላ ተመልሰን ንስሓ ልንገባ ስንል ደግሞ ዕድል አይሰጠንም። “ደክሞህ ነው፣ ሰክረህ ነው፣ አጥተህ ነው? መቼም ሰው ነህ ምን ታደርግ? አንተ ከማን ትበልጣለህ? ልጅነት ይዞህ ነው፣ ዕድሜህ ነው ወጣትነት ገፋፍቶህ ነው…” እና የመሳሰሉትን ማደንዘዣዎች እያመለከተው ለኃጢአቱ ጠበቃ እንዲያቆም ያደርገዋል። “ዓይንህ ብታሰናክልህ አውጥተህ ከአንተ ጣላት፤ ሁለት ዓይን ኖሮህ ወደ ገሃነመ እሳት ከምትጣል ይልቅ አንዲት ዓይን ኖራህ ወደ ሕይወት መግባት ይሻልሃል።” (ማቴ. ፲፰፥፱) እንደተባለው ጠቃሚ የሰውነታችን ክፍል እንኳ ሳይቀር እንዲሁም አካላችን የሆነው/ቺው ባል ወይም ሚስት እንኳ የድኅነት መንገዳችን ላይ እንዲቆሙብን አንፈቅድላቸውም። ስለዚህ ለሰይጣን በር ባለመክፈት የሰይጣንን ማታለያዎች ዐውቆ በእምነት መቃወም ይገባል እንጂ ለራስ ይቅርታ እያደረጉ ራስን ማታለል አይገባም።

፫. ራስን ማነጻጸር:- በኑዛዜ ወቅት የራስን ኃጢአት ከሌሎች ሰዎች ኃጢአት ጋር፣ ከዘመኑ ሁኔታ ጋር፣ ቀድሞ ከነበረበት ክፉ ግብር ጋር ማነጻጸር ተገቢ አይደለም። እኔ ገንዘብ ነው የሰረቅኩት አሉ አይደል እንዴ ሰውን የሚገድሉት! እኔ በጠላ ነው የሰከርኩት፤ አሉ አይደል እንዴ በጫት የሚሰክሩት! እኔ ከአንድ ሴት ጋር ነው የወደቅኩት፣ አሉ አይደል ሴቶችን የሚያተራምሱት! ቄሱና መነኩሴው እንደዚህ ይሠሩ የለ! ታዲያ ምእመኑ ይህንን ሁሉ ኃጢአት ሲሠራ እኔ ላይ ሲሆን ለምን እንደ ኃጢአት ይቆጠርብኛል? በማለት ራስን ከንስሓ ማራቅ ለኃጢአት መገዛትን ነው የሚያሳየው፡፡

ሰው የሚፈረድበት በግሉ ነው፣ ሰው ሁሉ የራሱን ሸክም ይሸከማል።  “እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ።” እንዳለው። (ራእ. ዮሐ. ፳፪፥፲፪)። ሰው ከማንም ጋር በኃጢአት ራሱን ማነጻጸር የለበትም። እንደ ቅዱስ ዳዊት ” እኔ መተላለፌን አውቃለሁና፥ ኃጢአቴም ሁል ጊዜ በፊቴ ነውና።ነውና” ማለት አለበት እንጂ።(መዝ. ፶፥፫)።

፬. በእግዚአብሔርን ቸርነት ማመካኘት:- እግዚአብሔር ንስሓ እንድንገባና ከኃጢአት እንድንላቀቅ ይታገሳል። “እግዚአብሔር ዓለምን ሁሉ በስድስት ቀን ፈጥሮ ጨርሶ ለንስሓ ግን መቶ ሃያ ዓመት ሰጠ” እንዳለ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ። ጠባቂ መልአክም “በዚህች ዓመት ደግሞ ተዋት” (ሉቃ. ፰፥፫) እያለ ይማልድልናል። ነገር ግን “የእግዚአብሔር ቸርነት ወደ ንስሓ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግሥቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን? (ሮሜ. ፪፥፬) እንደተባለው በቸርነቱ አመካኝቶ በኃጢአት ላይ ኃጢአት መጨመር እግዚአብሔርን መገዳደር ነው። “እግዚአብሔር ቸር ነው እያልክ በኃጢአት ላይ ኃጢአት አትጨምር” (ሲራክ ፭፥፭) እንዳለው ጠቢቡ ሲራክ የተጨመረልንን ጊዜ ለንስሓ ልናውለው ይገባል።

፭. ማፈር:- ሰው ማፈር ያለበት ኃጢአት ሲሠራ እንጂ ንስሓ ሲገባ ማፈር የለበትም። በእግዚአብሔር ፊት ከማፈር በአንድ ሰው (በንስሓ አባት) ፊት ማፈር ይሻላል። ይኸውም ከንስሓ አባት ጋር ተገቢ ባልሆነ መቀራረብ እና ከመጠን ባለፈ መደፋፈር ሊመጣ ይችላል። ከዚህም የተነሣ ‘ንስሓ አባቴ እኔን የሚያውቁኝ ቤተ ክርስቲያንን እንደምረዳ ነው፣ ደግ እንደሆንኩ ነው እንዴት ብዬ ኃጢአተኛ ነኝ እላቸዋለሁ?” በማለት በኑዛዜ ወቅት ታላላቅ ኃጢአቶችን ትተን ጥቃቅኑን ብቻ ለመናገርም ልንገደድ እንችላለን። በንስሓ ወቅት በካህን ፊት በስሜት ተገፋፍቶ ‘ደግሜ ኃጢአት ብሠራ’ ብለው መማል እና መገዘት ሌላ ጊዜ በተመሳሳይ ከወደቁ ተመልሶ በንስሓ አባት ፊት ሊያሳፍር ይችላልና መጠንቀቅ ያስፈልጋል። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “ከኃጢአት ጋር እየተጋደላችሁ ገና ደምን እስከ ማፍሰስ ድረስ አልተቃወማችሁም” (ዕብ. ፲፪፥፬) እንዳለው የጽድቅን መንገድ በጽኑ መከተል ይገባል።

፮. የጊዜ ቀጠሮ መስጠት:- በመጽሐፍ “ለነገ አትበሉ ነገ ለራሱ ያስባልና” (ማቴ. ፮፥) ይላል። ነገ ንስሓ እገባለሁ ፣ ዕድሜዬ ገና ነው ብለን የጊዜ ቀጠሮ መስጠት የሰይጣንን ዓላማ ለማሳካት መጣር ነው ምክንያቱም የሰይጣን ዓላማ የጊዜ ቀጠሮ እየሰጠ ንስሓ ሳንገባ (ኃጢአታችንን ሳንናዘዝ) እንድንሞትለት ነውና። ሰው ከኃጢአት ንጹሕ ሆኖ ስለማይገኝ ንስሓ ሁል ጊዜ የሚፈጸም እንጂ የጊዜ ቀጠሮ የሚሰጠው አይደለም። ቤተ ክርስቲያን የሁል ጊዜ ጥሪዋ  “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ” የሚለው ነው።

፰. ተስፋ መቁረጥ:- ደግመን ኃጢአት ብንሠራ ተስፋ መቁረጥ አይገባም ደግመን በንስሓ ሳሙና መታጠብና ኃጢአትን ማስወገድ እንጂ። ኃጢአት እንደ እሾህ ነው፤ እሾህ የወጋው ሰው ወዲያው ይነቅላል እንጂ ትንሽ ይቆይ ብሎ እንደማያቆየው ሁሉ ኃጢአትንም ያለ ቀጠሮ ወዲያው መናዘዝ ይገባል። ተስፋ መቁረጥና መሰላቸት ብዙዎችን ከንስሓ ሕይወት ያርቃቸዋል። እግዚአብሔር እኛን ይቅር ማለት ሳይሰለች እኛ ግን ማረን ይቅር በለን ማለት ይሰለቸናል። የሰይጣን ትልቁ ዓላማ ሰውን ተስፋ ማስቆረጥ ነው። ነገር ግን “እግዚአብሔርን ተስፋ የሚያደርጉ አያፍሩም” (መዝ. ፳፭፥፫) በእግዚአብሔር ተስፋ መቁረጥ ተገቢ አይደለም። “ተስፋ አያሳፍርም” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (ሮሜ. ፭፥፭) በነቢዩ ቃል “የወደቀ አይነሣምን? የሳተስ አይመለስምን?” ብለን ልናሳፍረው ይገባል። (ኤር.፰፥፬)። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “መውደቅ አዳማዊ ነው ወድቆ አለመነሳት ግን ዲያብሎሳዊ ነው” እንዳለው ወድቆ ሳይነሣ ምውት ሆኖ የቀረው ዲያብሎስ ብቻ ነው። “ንስሓ በገባህበት ሥራህ የምትጸጸት አትሁን” እንዳለው ቅዱስ ቀሌምንጦስ ዘሮም ንስሓ በገባንበትና ቀኖና በተቀበልንበት ኃጢአት መጨነቅ፣ እግዚአብሔር ይቅር ይለኝ ይሆን? ማለት አይገባም። የእኛ ኃጢአት የእግዚአብሔርን ምሕረት አይሸፍነውምና።

የንስሓ በረከቶች

፩. የኃጢአት ስርየት ይገኛል

ትልቁ ስጦታ የኃጢአት ስርየት ማግኘት ነው።  “እንግዲህ ከጌታ ፊት የመጽናናት ዘመን እንድትመጣላችሁ አስቀድሞም ለእናንተ የመረጠውን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዲልክላችሁ፥ ኃጢአታችሁ ይደመሰስ ዘንድ ንስሓ ግቡ ተመለሱም።” (ሐዋ. ፫፥፲፱-፳)። ንስሓ በኃጢአት የዛገውን እንደ ወርቅ ታጠራዋለች። ቅዱስ ጴጥሮስን ከወደቀበት አንሥታ ሊቀ ሐዋርያት እንዳደረገችው ማለት ነው።

፪. ሕይወት ይገኛል

ንስሓ ሕይወትን ታሰጣለች። “ወደ ሕይወት ልትገባ ብትወድስ ትእዛዛትን ጠብቅ” እንዲል፡፡ (ማቴ.፲፱፥፲፯)

፫. መንፈሳዊ አባት(እረኛ) ይገኛል

ሰው ደካማ ስለሆነ በመንፈሳዊ ሕይወቱ እንዲበረታ፣ ቢበድል ኃጢአቱን በመናዘዝ ስርየትን ያገኝ ዘንድ፣ ከእግዚአብሔርም ጋር ይታረቅ ዘንድ መንገዱንም የሚመራ መንፈሳዊ አባት ያስፈልገዋል፡፡ ምእመናን ካህንን ስለ ሁሉም ነገር ማማከር ይገባቸዋል፣ የማሰርና የመፍታት ሥልጣን ተሰጥቷቸዋልና፡፡ (ማቴ. ፲፰፥፲፰) ጌታችን በወንጌል “በቀን የሚመላለስ ቢኖር የዚህን ዓለም ብርሃን ያያልና አይሰናከልም በሌሊት የሚመላለስ ቢኖር ግን ብርሃን በእርሱ ስለሌለ ይሰናከላል።”(ዮሐ. ፲፩፥፱-፲) ብሏል። ‘የዚህ ዓለም ብርሃን’ የተባሉት “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ” የተባሉት ካህናት ሲሆኑ በቀን የሚሄድ የተባለው በምክረ ካህን የሚኖር ማለት ነው። በምክረ ካህን መኖር በትዳርና በማኅበራዊ ኑሮ ችግሮችን ለመፍታት ይረዳል። ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው “የትዳር ጉዳይ ይቅርና በመላእክት እንኳ እንድንፈርድ አታውቁምን?” (፩ቆሮ. ፮፥፫-፮) የካህናት ሥልጣን እስከምን ድረስ እንደሆነ ያስረዳል።

ንስሓ አለመግባት የሚያስከትለው ጉዳት

“የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና”(ሮሜ ፮፥፳፫) እንደሚል ሰው በኃጢአት ምክንያት አራት ዓይነት ሞቶች ያገኙታል:-

አንደኛ በበሽታ ጤናው ተቃውሶ የሥጋ ሞት ያገኘዋል። ሁለተኛው መልካም ምግባራት ይርቁትና የሥነ ምግባር ሞት ያገኘዋል።  ሦስተኛ የሥጋ ሞት ያገኘዋል። አራተኛ የዘለዓለም ሞት ያገኘዋል። ነቢዩ ሕዝቅኤል “ኃጢአትን የምትሠራ ነፍስ እሷ ትሞታለች”(ሕዝ. ፲፰፥፬) እንዳለው ማለት ነው። የዚህ ዓለም ሥቃይ ማብቂያ አለው። በዚህ ዓለም ለአምላኩ ብሎ የተሠቃየ ሰው በወዲያኛው ዓለም ያርፋል። በሞት የማያርፉት ሞት ግን የዘለዓለም ሞት ነው።

በአጠቃላይ ንስሓ ዲያብሎስን ከሚያስመስል ከጨለማ ሥራ ተላቆ እግዚአብሔርን የሚያስመስለውን የጽድቅን ሥራ መሥራት ነው። እግዚአብሔር ከጽድቅ እና ከጻድቃን ጋር ይተባበራል። ከኃጥኣንና ከኃጢአት ጋር ደግሞ ኅብረት የለውም። እኛም እግዚአብሔርን የሚያስመስለውን የጽድቅ ሥራ መሥራት ይገባናል? ንስሓ በምድር ላይ ሰላማዊ ሕይወት እንድንኖርና በሰማይም ዘለዓለማዊ ዕረፍትን የምታጎናጽፍ መንፈሳዊ ሕክምና ናት። የሕክምና ሂደቷም ዘርፈ ብዙ የጎንዮሽ ጥቅም እንጂ ፍጹም የጎንዮሽ ጉዳት የሌላት ሕክምና ናት። ስለዚህም ዕድሜያችን ኃጢአት ለመሥራት የደረስን ሁላችንም ለአቅመ ንስሓም ደርሰናልና ለነገ ሳንል ኃጢአታችንን ለንስሓ አባታችን ተናዝዘን ቀኖናችንን በአግባቡ ፈጽመን ቅዱስ ሥጋውን በልተን ክቡር ደሙን ጠጥተን የመንግሥቱ ወራሾች የክብሩ ቀዳሾች እንድንሆን የአምላካችን ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት የቅዱሳን ሁሉ ጸሎት ያግዘን። አሜን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሰሙነ ሕማማት (ሰኞ)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰሙነ ሕማማትን ከሌሎቹ የዐቢይ ጾም ሳምንታት በተለየ ሁኔታ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ለመከራ ተላልፎ የተሰጠበትንና አዳምና ልጆቹን ያድን ዘንድ በዕለተ ዓርብ በፈቃዱ በመስቀል ላይ መሰቀሉን በመስበክ ሕማሙንና ስቃዩን እያሰበች በጾም፣ በጸሎትና በሐዘን ታከብረዋለች፡፡ ምንባባቱ፣ የዜማ ክፍሎቹ ሁሉ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምንም በደል ሳይገኝበት አይሁድ በምቀኝነት ተነሣስተው ያደረሱበትን ስቃይ፣ በመስቀል ላይ እርቃኑን በቀራንዮ አደባባይ እንደ ሰቀሉት፣ ሞቱንና ወደ መቃብር መውረዱንና በሦስተኛውም ቀን ሞትን በሥልጣኑ ድል ነሥቶ መቃብር ክፈቱልኝ፣ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል በራሱ ሥልጣን ሞትን ድል አድርጎ መነሣቱን፣ በትንሣኤውም ትንሣኤአችንን እንዳበሰረ የሚነገርበት ነው፡፡

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት በሰሙነ ሕማማት ከጸሎተ ሐሙስ በስተቀር ቅዳሴ አይቀደስም፤ ስብሐተ ነግህ አይደረስም፤ ጸሎተ ፍትሐት አይጸለይም፤ ጸሎተ አስተስርዮም አይደረግም፣ ጥምቀተ ክርስትናም አይፈጸምም፡፡ እነዚህም አስቀድሞ በዕለተ ሆሣዕና ይከናወናሉ፡፡ በተጨማሪም በሰሙነ ሕማማት ምእመናን መስቀል እንደማይሳለሙት ሁሉ መጨባበጥ፤ መሳሳምና የትከሻ ሰላምታ መለዋወጥን አይፈጽሙም፡፡ ሰላምታ የማንለዋወጥበት ምክንያት አይሁድ ጌታን ለመስቀል ሰኞ እና ማክሰኞ መከሩ አልሰመረላቸውም፡፡ ምክራቸው የተፈጸመው ረቡዕ ነው፡፡ ማንኛውም ክብረ በዓል በዚህ ሳምንት ቢውል ከትንሣኤ በኋላ ይከበራል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰሙነ ሕማማት ባሉት አምስት ቀናት ማለትም ከሰኞ እስከ ዓርብ ስቅለቱ ያከናወናቸውን ሥራዎች ቅድሚያ ሰጥተን በዚህ ጽሑፋችን ከፋፍለን እንመለከታለን፡፡ 

ሰኞ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ሆሣዕና ለኢየሩሳሌም ቅርብ ወደሆኑት ወደ ደብረ ዘይትና ወደ ቤተ ፋጌ ደርሶ በተናቁትና ሮጠው ማምለጥ በማይችሉት በአህያይቱና ውርንጫይቱ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሕዝቡ እና ሕፃናቱም ልብሳቸውን እያነጠፉ፣ የወይራና የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው “ሆሣዕና በአርያም፤ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው” እያሉ አመስግነውታል፡፡ “ከልጆችና ከሕፃናት አንደበት ምስጋናን አዘጋጀህ” ተብሎ እንደተጻፈ እያመሰገኑት ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ በዚያም ታላላቅ ተአምራትን አድርጎ፣ በቤተ መቅደስ የሚሸጡንና የሚገዙትን ሁሉ አባረረ፤ የገንዘብ ለዋጮችና ርግብ ሻጮችን መደርደሪያና ወንበር ገልብጦ “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል ተብሎ ተጽፏል እናንተ ግን የሌባና የቀማኛ ዋሻ አደረጋችሁት” አላቸው፡፡ ትቷቸውም ወጥቶ ወደ ቢታንያ ሄዶ እንዳደረ ቅዱስ ማቴዎስ ይተርክልናል፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፩-ፍጻሜ)

በማግሥቱም (ሰኞ) ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ከተማ ሲመለስ ተራበ፡፡ ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን ዕፀ በለስ አግኝቶ ፍሬ አልባ ሆና ነገር ግን ቅጠል ብቻ ሆና አግኝቷታልና “እንግዲህ ወዲህ ለዘለዓለም ፍሬ አይኑርብሽ” በማለት ረገማት፤ ወዲያም በለሲቱ ደረቀች፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፲፰-፲፱) 

ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ አምላክ ሲሆን፣ ከሦስቱ አካላት በሥጋ ማርያም ማኅፀን በኅቱም ድንግልና ገብቶ በኅቱም ድንግልና ተወልዶ፣ በሥጋ ተገልጦ በዚህች ምድር ላይ እየተመላለሰ ሲያስተምር “የእኔስ መብል የላከኝን የአባቴን ፈቃድ አደርግ ዘንድ፤

ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው” ብሎ ተናግሯል (ዮሐ. ፬፥፴፬)፡፡ ታዲያ ጌታችን ለምን ተራበ?

ቅዱስ ማቴዎስ እንደተራበ ሲገልጽ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ደግሞ ቀድሞ በትንቢቱ “እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም” ብሏል (ኢሳ. ፵፮፥፳፭)፡፡ ይህን እንዴት ያስታርቁታል ቢሉ፡- ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ “በመጀመሪያ ቃል ነበረ፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ፤ ይህም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፡፡ ሁሉም በእርሱ ሆነ፤ ከሆነውም ሁሉ ያለ እርሱ ምንም የሆነ የለም፡፡”  ሲል ጽፏል (ዮሐ. ፩፥፩-፫)፡፡ ሰማያውያን መላእክት እንዳይራቡ አድርጎ የፈጠረ፤ እስራኤልን ገበሬ በማያርስበት፣ ዘር በሌለበት፣ ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ የመገበ፤ ድኅረ ሥጋዌ በአምስት አንጀራና በሁለት ዓሣ ከአምስት ሺሕ የሚበልጡ ሰዎችን የመገበ ጌታ “ተራበ” ተብሎ ሲነገር እጅግ ይደንቃል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው በመሆኑ አልተራበም፣ አልተጠማም አንልም፡፡ የጌታችን ረኃብ ግን የድህነት (የማጣት) አይደለም፡፡ የክርስቶስ ረኃቡ የበለስ ፍሬ ሳይሆን ከሰው ልጆች ዘንድ ሃይማኖትና የመልካም ሥነ ምግባርን ፍሬ አፍርተው አለማግኘቱን ለማጠየቅ ነው፡፡ ለዚህም “ተራበ” ተባለ፡፡ በዚህም ምክንያት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእሥራኤል (አይሁድ) የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረግሟል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በአይሁድ ጉባኤ የነገሠውን ኃጢአት፤ በበለስ አንጻር መርገሙን ሲገልጽ “በበለስ አንጻር ኃጢአትን ረገማት” ብሏል፡፡ እስራኤልም ጌታችን የጠበቀባቸውን ፍሬ ባለማፍራታቸው ተረግመዋል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እስራኤል ከፍቅር ይልቅ እርግማን እንዳገኛቸው፤ አሕዛብ ደግሞ የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው ያመኑበትን የእግዚአብሔር የጸጋ ልጁ ለመሆን መብቃታቸውን መስክሯል፡፡ በተጨማሪም “አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾሁ ተረፈ፤ ይኸውም የሃይማኖት ጉድለት ነው” ብሎ ተርጕሞታል፡፡ እሾኽ የእርግማን፤ አበባ የእግዚአብሔር ጸጋ ልጅነት ምሳሌ ነው፡፡

ጌታችን ወደ መቅደስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይሆን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል “ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤” ይለናልና እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገውን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ አፍርተን እንገኝ ዘንድ ዘወትር መትጋት ይገባል፡፡ (ማቴ. ፫፥፰፤ ገላ. ፭፥፳፪)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር