ቃና ዘገሊላ

ይህ በዓል ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከዘጠኙ ንዑሳን በዓላት መካከል አንዱ ሲሆን ይህም ጥር ፲፪ቀን ይውላል፡፡ የቃና ዘገሊላ ጥንተ ነገሩ ወይም ታሪኩ የተፈፀመው የካቲት ፳፫ ቀን ነው፡፡ ነገር ግን አባቶቻችን የውኃን በዓል ከውኃ በዓል ጋር ለማክበር ብለው የየካቲቱን በዓል ወደ ጥር ፲፪ አምጥተውታል፡፡ ይህም ውኃ ወደ ወይን የተለወጠበትን በዓል ከጌታ ጥምቀት በዓል ጋር በማስተሳሰር ለማክበር ነው፡፡ (ስንክሳር ዘጥር ፲፪)

“በሦስተኛውም ቀን በገሊላ ቃና ሠርግ ነበረ፥ የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች፤ ኢየሱስም ደግሞ ደቀ መዛሙርቱም ወደ ሠርጉ ታደሙ። የወይን ጠጅም ባለቀ ጊዜ የኢየሱስ እናት፡- “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” አለችው። ኢየሱስም፡- “አንቺ ሴት፥ ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም” አላት። እናቱም ለአገልጋዮቹ፡- “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ” አለቻቸው። አይሁድም እንደሚያደርጉት የማንጻት ልማድ ስድስት የድንጋይ ጋኖች በዚያ ተቀምጠው ነበር፥ እያንዳንዳቸውም ሁለት ወይም ሦስት እንስራ ይይዙ ነበር። ኢየሱስም፡- “ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው” አላቸው። እስከ አፋቸውም ሞሉአቸው። “አሁን ቀድታችሁ ለአሳዳሪው ስጡት” አላቸው፤ ሰጡትም። አሳዳሪውም የወይን ጠጅ የሆነውን ውኃ በቀመሰ ጊዜ ከወዴት እንደ መጣ አላወቀም፤ ውኃውን የቀዱት አገልጋዮች ግን ያውቁ ነበር፤ አሳዳሪው ሙሽራውን ጠርቶ፡- ሰው ሁሉ አስቀድሞ መልካሙን የወይን ጠጅ ያቀርባል፥ ከሰከሩም በኋላ መናኛውን፤ አንተስ መልካሙን የወይን ጠጅ እስከ አሁን አቆይተሃል?” አለው። ኢየሱስ ይህን የምልክቶች መጀመሪያ በገሊላ ቃና አደረገ፤ ክብሩንም ገለጠ፥ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ።”(ዮሐ. ፪፥፩-፲፩)።

ሦስተኛ ቀን ምንድን ነው?

፩. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀው ጥር ፲፩ ቀን ነው፡፡ ወዲያውኑ እንደተጠመቀ ሳይውል ሳያድር ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሄደ፤ ፵ ቀንና ፵ ሌሊት ጾመ፤ ጾሙ የካቲት ፳ ቀን ቅዳሜ ይፈጸማል፡፡ ለእሁድ ሦስተኛ ቀን የካቲት ፳፫ ቀን ማክሰኞ በሦስተኛው ቀን ሠርግ ነበር፡፡

ሦስተኛ ቀን የሚለው፡-

  • የመጀመሪያ ቀን የሚባለው ዘመነ አበው፤ አዳም፤ እነአብርሃም፤ ይስሐቅ አበው የነበሩበት ዘመን ሲሆን፤
    •  ሁለተኛ ቀን የሚባለው ዘመነ ኦሪት ነው፤ እነሙሴ የነበሩበት ዘመን፣
    •  ሦስተኛ ቀን የተባለው ዘመነ ሐዲስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የሆነበት ዘመን ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ነበር ሠርግ የሆነው።

፪.ጌታችን  ፊልጶስን  አግኝቶ  “ተከተለኝ”  ካለበትና  ፊልጰስም  ጓደኛውን  ናትናኤልን  ከጠራበት  ዕለት  ሦስት  ቀን በኋላ ተአምሩን አደረገ  ነው፡፡ (ዮሐ. ፩፥፵፬) 

፫.በነገው ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ቆመው ነበር። ያለውን እሑድ (ዮሐ. ፩፥፴፭)፣ በነገው ኢየሱስ ወደ ገሊላ ሊወጣ ወደደ፥ ፊልጶስንም አገኘና ተከተለኝ አለው (ቁ.፵፬) ያለውን ሰኞ ብሎ በመተርጐም ማክሰኞ  ተአምሩን  በቃና  አደረገ  የሚል  ነው፡፡

፬. የእኛ ቤተ ክርስቲያን የበለጠ  የምታስተምረው አገባብ ደግሞ ጌታችን  በዮሐንስ  እጅ ከተጠመቀ በኋላ  ሳይውል  ሳያድር ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሔዶ የጾመውን ዐርባ ቀንና ሌሊት  እንደ  አንድ  ቀን በመቁጠር ከዚያ  መልስ  ተአምራቱን አደረገ  የሚል  ነው፡፡ (ቃና ዘገሊላ፤ ዲ/ን ሔኖክ ኃይሌ)

ዐርባ ቀንና ሌሊት እንደ አንድ ቀን እንዴት ይቆጠራል? ቢባል ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ልማድ ስለሆነ ነው፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ማቴዎስ “ጌታችን ከግብፅ ስደት መልስ ወደ ናዝሬት መጥቶ ኖረ” ብሎ ከጻፈ በኋላ ቀጥሎ በዚያም ወራት መጥምቁ ዮሐንስ፡- መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ ብሎ በይሁዳ ምድረ በዳ እየሰበከ መጣ ብሎ ጽፎአል፡፡ (ማቴ. ፪፥፳፫፤ ፫፥፩) በሁለቱ ዓረፍተ ነገሮች መካከል የሃያ አምስት ዓመታት ልዩነት  አለ፡፡ ብዙውን እንደ አንድ መቁጠር የመጻሕፍት ልማድ ስለሆነ “በዚያ ወራት” ብሎ ጻፈ፡፡ ይህ የትርጓሜ አገባብ የበለጠ ትርጒም የሚሰጥ ነው፡፡ ከማንኛውም መንፈሳዊ  አገልግሎትና ተአምራት በፊት  መጾምና  መጸለይ

እንደሚቀድም ያስተማረንም  ከቃናው  ተአምር በፊት በገዳመ ቆሮንቶስ በመቆየቱ ነው፡፡

የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች

  • ቤተ ዘመድ ናትና ተጠርታ።
  • እመቤታችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሥጋዊ ዕድገቱ እንደምትቀድመው ሲያጠይቅ። እንኳን የእርሱ እናት ትቅርና ዮሐንስ መጥምቁም በ፮ ወር ይቀድመው ነበር፡
  • አስቀድማ የነበረችውንና ከኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን በፊት የኖረችውን ድንግል ማርያምን ሳናውቅ ኢየሱስን እናውቃለን ማለት አይቻልም ሲል፡፡

ወይኑ ባለቀ ጊዜ “ወይን የላቸውም” አለች፡፡

የወይኑን ማለቅ ለእመቤታችን ማን ነገራት? ሙሽራው ወይስ ከሠርገኞቹ መካከል አንዱ? ለዚህ ምንም ዓይነት መልስ እንደማይሰጥ ግልጽ ነው፡፡ ድንግል ማርያም ግን ራሷ ነበር ያወቀችው፤ ነቢይት ናትና፡፡ ስለሆነው እንዲሁም ስለሚሆነው ታውቃለች፤ ቅዱስ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ካመሰገኗት በኋላ “ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብጽዕት ይሉኛል” ማለቷ ወደፊት ስለሚመጣው ትውልድ ነበር የተናገረችው፤ ይህ ነቢይነቷን የሚገልጽ ነው፡፡ (ሉቃ. ፩፥፵፰-፵፱)

ኢሳይያስ በትንቢቱ “ወደ ነቢይቱ ሄድኩ ጸንሳም ነበር” (ኢሳ. ፰፥፩) የሚላት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ነው፡ በሶርያ የነበረው ንጉሥ በኢየሩሳሌም ያለውን ንጉሥ ሊወጋ (ሊገድል) በፈለገ ጊዜ በእልፍኝ ሆኖ የሚመክረውን ምክር ነቢዩ ኤልሳዕ ኢየሩሳሌም ሆኖ ይመለከትና ያውቅ ነበር፤ ኢየሩሳሌም ሆኖ በሶርያ የሚደረገውን እያየ ነበር፡፡ ስለዚህም የኢየሩሳሌሙን ንጉሥ “ከቤትህ እንዳትወጣ ሶርያውያን ሊገድሉህ ይፈልጋሉ” (በ፩ኛ ነገ. ፮፥፰) እያለ ይመክረው ነበር፡፡ ምን ዓይነት ጸጋ እንደሆነ አስቡት፤ ኢየሩሳሌም ሆኖ በሶርያ የሚደረገውን ነገር ማወቅ፡፡ ታዲያ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ነቢያት እንዲህ የርቀቱን ነገር የሚያውቁ ከሆነ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የዶኪማስን የቤት ችግር፤ የወይን ማለቅ ብታውቅ ብትረዳ ምን ይደንቅ። የመለኮት እናትም እንዴት ጸጋው ይበዛላት፤ እንደ እመቤታችንስ ጸጋው የበዛለት በዘመነ ብሉይ ማን ነበር። “ጸጋን የተመላሽ ድንግል ሆይ ደስ ይበልሽ” የተባለች ድንግል ማርያም አይደለችምን?

“ከአንቺ ጋር ምን አለኝ”

፩. “ያልሽኝን እንዳልፈጽምልሽ ምን የሚከለክለኝ ነገር አለ” ሲል ነው፡፡ “እናትና አባትህን አክብር፤ ለእናትና ለአባትህ ታዘዝ” ያለ አምላክ እናቱን ሂጂልኝ፤ ወግጅልኝ አላት ሲባል አያሳፍርም? ይህማ እንዳይሆን “ለእናቱ እየታዘዘ አደገ” ወንጌል ይል የለምን፡፡ (ሉቃ. ፪፥፶፩)

፪. ውኃውን ጠጅ አድርግላቸው ብትዪኝ አይሆንም እልሽ ዘንድ ውኃውን ጠጅ ላላደርግላቸው ከሠርግ ቤት ተጠርቼ መጥቻለሁን? ውኃውን ጠጅ ላደርግላቸው ነው።

፫. በአምላክነቱ አገብሮ ተአዝዞ እንደሌለበት ለማጠየቅ

“ጊዜዬ ገና አልደረሰም”

፩. ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ አለውና በቀትር የሚሠራውን በሠለስት አይሠራም፤ በሠለስት የሚሠራውን በነግህ አይሠራምና።

፪. ወይኑ ከእንስራው ፈጽሞ አላለቀም ነበር። ያለውን አበርክቶት ቢሆን ያኑ አበረከተው ተብሎ ተአምራቱ ድንቅ ባልተባለ ነበርና።

፫. ይሁዳ ወጥቶ ነበርና ከተአምራቱ ቢለየኝ ከሞቱ ገባሁበት እንዳይል።

፬. ለዓለም ቤዛ የምሆንበት፣ በመስቀል ላይ የምሰቀልበት ሰዓቱ ገና ነው ሲል ይህን ተናገረ። (ትርጓሜ ወንጌል ዘዮሐንስ ፪፥፬)

የሠርጉ ባለቤት ማን ነበር?

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ሙሽራው ማን እንደሚባል እና ሙሽራዋም ማን እንደሆነች የሚገልጽ የለም። በግብረ ሕማማት ረቡዕ ምሽት ሦስት ሰዓት ምንባብ ላይ በሚገኘው ተዓምረ ኢየሱስ የሙሽራው ስም ዶኪማስ እንደሆነ ይናገራል። ስለ ሙሽራዋ ግን ምንም አይገልጽልም። የተዓምሩ ክፍል እንድህ ይላል፦

“ናትናኤልም ባቲላስ በሚባል አገር ሳለ ይህችውም በገሊላ አውራጃ የምትገኝ የቃና ምድር ናት። በዚያች በቃና ሠርግ በተደረገ ጊዜ ጌታችን ወደ ሠርጉ ግብዣ ይመጣና ይባርካቸው ዘንድ ናትናኤል ለምኖ እንዲያመጣው ዘመዶቹ ማለዱት፤ የሙሽራውም ስሙ ዶኪማስ ይባላል። እርሱም የዮካን ልጅ ነው። ናትናኤልም ወደ ጌታ ኢየሱስ ሂዶ “ጌታችን ሆይ የአባቴ የወንድም ልጅ ወደሆነው ወደ ዶኪማስ ሠርግ ትመጣልን ዘንድ የሠርጉንም ቤት ትባርክ ዘንድ እለምንሃለሁ” አለው። ጌታችን ኢየሱስም ጥሪውን ተቀብሎ አብሮ ወደ ሠርጎ ቤት ሄደ። ወደዚያም በገባ ጊዜ በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ማርያም እና ሰሎሜ ወደ ሠርጉ ይመጡ ዘንድ ሰው ተላከ እነሱም መጡ” ይላል። (ተአምረ ኢየሱስ)

በተአምረ ኢየሱስ አገላለጽ ሙሽራው የሐዋርያው የናትናኤል አጎት የዮካን ልጅ ዶኪማስ ነው። ሌላው ወንጌላዊው የቅድስት ሰሎሜን መገኘት ያልጻፈ ቢሆንም ከድንግል ማርያም ጋር በሠርጉ ቤት ታድማለች። ይህን መሠረት በማድረግ ትርጓሜ ወንጌል የእመቤታችንን በሠርጉ መገኘት “ቤተሰብ ነች” በማለት ይገልጻል። (ትርጓሜ ወንጌል ዘዮሐንስ ፪፥፩)

የቅዱስ ሚካኤል በዓል እንዴት አብሮ ይከበራል?

ቅዱስ ሚካኤል እስራኤል የተባለ ያዕቆብ ከወንድሙ ከኤሳው ጋር ተጣልቶ ፈርቶ ሳለ የረዳው እና ዮርዳኖስን አሻግሮት ወደ እናቱ ወንድም ወደ ላባ ሄደ። ያዕቆብ የአጎቱን ልጆች ልያንና ራሔልን አግብቶ ብዙ ገንዘብ እና ልጆች አፈራ። በኋላም ከንብረቱ እና ከልጆቹ ጋር ቅዱስ ሚካኤል መንገድ እየጠረገና እያቀና ወደ አገሩ በሰላም መለሰው። ወንድሙ ኤሳውም በፍቅር ተቀበለው። ቅዱስ ሚካኤል ለያዕቆብ ዮርዳኖስን ከፍሎ ያሻገረበትን መታሰቢያ “የውኃን በዓል በውኃ” ለማክበር አባቶች ሥርዓት ሠርተው እናከብራለን።

ጥምቀት

የጥምቀት ትርጉም እና ምንነት

ጥምቀት ማለት አጥመቀ(አጠመቀ) ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም መነከር፣ መጥለቅ፣ መደፈቅ፣ በውኃ ውስጥ መጠመቅ ማለት ነው። በሌላ አገላለጽ፡- ጥምቀት አስተርእዮ ወይም መገለጥ  ማለት ነው። (ነገረ ሃይማኖት ዘተዋሕዶ ገጽ ፻፵፭)። በግሪክ ደግሞ ኤጲፋንያ ሲባል ትርጓሜውም መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው (ስንክሳር ዘጥር ፲፩)።ይህም የእግዚአብሔር አንድነት እና ሦስትነት የተገለጠበት ታላቅ ምሥጢር መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ እግዚአብሔር የሦስትነቱን ምሥጢር ገልጦበታልና አብ ከሰማይ ሆኖ “የምወደው፣ በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” (ማቴ. ፫፥፲፮-፲፯) እያለ ሲመሰክር ወልድም በዕደ ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ ሲጠመቅ፣ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል በራሱ ላይ ሲቀመጥ ታየ ወይም ተገለጠ። 

ጥምቀት የሰው ልጆች ሁሉ ከአዳም ጀምሮ የወረስነውን ኃጥአት ደምስሶ በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን እንጠራና ዳግም እንድንወለድ የሚያደርገን የመጀመሪያው ምሥጢር የተፈጸመበት ነው። የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከምሥጢራት ሁሉ አስቀድሞ የፈጸመው ታላቅ ምሥጢር ነው። ስለዚህ ከምሥጢራት ሁሉ ጥምቀት ይቀድማል። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን ከመምረጡ በፊት፣ ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሄዶ ከመጾምና ከመጸለዩ አስቀድሞ፣ ትምህርት ማስተማር እና ተዓምራት ከማድረጉ በፊት የመጀመሪያ ያደረገው በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ በመጠመቅ ምሥጢረ ጥምቀትን መሠረተ። የመንፈስ ቅዱስ ሱታፌ የሚገኘው በምሥጢረ ጥምቀት ነውና። ሥጋዊ ልደት አንድ እንደሆነ ሁሉ መንፈሳዊ ልደትም አንድ ጊዜ የሚፈጸም ነው። ስለዚህ ጥምቀት አይደገምም። “ጌታ አንድ ነው፣ ሃይማኖትም አንዲት ናት፣ ጥምቀትም አንዲት ናት” (ኤፌ. ፬፥፭)                                                      

ጥምቀተ ክርስቶስ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ መጠመቁን ሲያመለክት “ያን ጊዜ ኢየሱስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ።” በማለት ወንጌላዊው ማቴዎስ ይነግረናል፡፡ (የማቴ. ፫፥፲፫)

ጌታችንን የሚያጠምቀው መጥምቁ ዮሐንስ እንደሆነ በትንቢትም የተገለጠ ነው። ይህንንም ከዐበይት ነቢያት መካከል ኢሳይያስ “ የአዋጅ ነጋሪ ቃል፦ የእግዚአብሔርን መንገድ ጥረጉ፥ ለአምላካችንም ጐዳና በበረሃ አስተካከሉ።” (ኢሳ. ፵፥፫) ሲል፤ ወንጌላውያንም የትንቢቱን  ፍጻሜ አስተባብረው አረጋግጠውታል። “በነቢዩ በኢሳይያስ፦ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮህ ሰው ድምፅ የተባለለት ይህ ነውና።” (ማቴ. ፫፥፫) በማለት ሲገልጸው፤ “እነሆ፥ መንገድህን የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ፤ የጌታን መንገድ አዘጋጁ፤ ጥርጊያውንም አቅኑ፤ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ ተብሎ በነቢዩ በኢሳይያስ እንደ ተጻፈ፥” (ማር. ፩፥፪-፫)፤ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስም “በነቢዩ በኢሳይያስ ቃል መጽሐፍ፦ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፤ ዐዘቅቱ ሁሉ ይሙላ ተራራውና ኮረብታውም ሁሉ ዝቅ ይበል፥ ጠማማውም የቀና መንገድ ይሁን፥ ሸካራውም መንገድ ትክክል ይሁን፤ ሥጋም የለበሰ ሁሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ ተብሎ እንደ ተጻፈ ለኃጢአት ስርየት የንስሐን ጥምቀት እየሰበከ በዮርዳኖስ ዙሪያ ወዳለችው አገር ሁሉ መጣ።” (ሉቃ. ፫፥፫-፮)፤ “እርሱም፦ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለ፦ የጌታን መንገድ አቅኑ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ እኔ ነኝ አለ።” (ዮሐ. ፩፥፳፫) በዚህም መሠረት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በ፴ ዘመኑ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ፡፡

ጌታችን ለምን ተጠመቀ?

ጌታችን እንደ አይሁድ የመንጻት ልማድ ከኃጢአት ለመታጠብ አይደለም። እንደ ኃጥአን መጽብሐን ከዮሐንስ ዘንድ ለንስሓ እንደተጠመቁትም ጥምቀት አይደለም። (ዘሌ. ፲፭፥፩-፲፫፤ ማቴ. ፫፥፮) “በይሁዳና በኢየሩሳሌም፣ በዮርዳኖስም ያሉ ሰዎች ወደ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እየመጡ ኃጢአታቸውን እየነገሩት በዮርዳኖስ ያጠምቃቸው ነበር።” ምን እያለ ያጠመቃቸው ነበር? ቢባል “እገሌ ተጠመቅ በማየ ንስሓ ከመ ትኩን ረድኦ ለክርስቶስ፤ እገሌ ለክርስቶስ አገልጋይ ትሆን ዘንድ በንስሓ ውኃ ተጠመቅ” እያለ ያጠምቃቸው ነበር። (ትርጓሜ ወንጌል ዘማቴዎስ)።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ለምን ተጠመቀ?

፩. ለእኛ ሥርዓተ ጥምቀትን ለመመስረት (ዳግም ልደትን ለመስጠት)

፪. ትሕትናን ለማስተማር፦ ዮሐንስን መጥተህ አጥምቀኝ ከማለት ወይም ባሪያ ወደ ጌታው ከመሄድ ጌታ ወደ ባሪያው ሂዶ በባሪያው እጅ መጠመቁ ትሕትናውን ያመለክታልና። ጌታችን ወደ መጥምቁ ዮሐንስ መምጣቱ ለዮሐንስ ክብር ስለሆነው ክብሩን በሚገልጽ አገላለጽ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት ተባለ።

፫. ለአብነት፦ ጌታችን ዮሐንስን መጥተህ አጥምቀኝ ቢለው ነገሥታትና ካህናትን ወደ እኛ መጥታችሁ አጥምቁን እንዳይሉ ሂዳችሁ ተጠመቁ ለማለት አብነት ለመሆን።

፬. ዮርዳኖስን  ብርህት ማኅፀን ለማድረግ (ውኃን ለመባረክ)፦ ለጥምቀት ኃይል ለመስጠት

፭. አንድነቱንና ሦስትነትን ለመግለጥ ጌታችን ተጠመቀ፡፡

ለምን በዮርዳኖስ ተጠመቀ

፩. ትንቢቱን ለመፈጸም፡- “ባሕርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ግብአ ድኅሬሁ፤ ባሕር አየች ሸሸችም ዮርዳኖስም ወደ ኋላ ተመለሰ” (መዝ. ፻፲፫፥፫)

፪. ምሳሌውን አማናዊ ለማድረግ፦ ዮርዳኖስ ከላይ ነቁ አንድ ነው፣ የሰው ሁሉ ነቁ፤ መገኛው አንድ አዳም ነው። ዝቅ ብሎ በደሴት ለሁለት ይከፈላል። እስራኤል በግዝረት፣ አሕዛብ በቁልፈት መለያየታቸውን ያሳያል፤ ወረድ ብሎ ደግሞ ይገናኛል። ይህም ጌታ በጥምቀቱ ሕዝብና አሕዛብን አንድ ሊያደርግ መምጣቱን ያመለክታል።

፫. የዕዳ ደብዳቤያችንን ሊደመስስልን፦ ዲያብሎስ መጋረጃ ጋርዶ በአዳም እና በሔዋን መከራን አጸናባቸው። ስመ ግብርናታችሁን ጽፋችሁ ብትሰጡኝ አቀልላችኋለሁ አላቸው። “አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ፤ ሔዋን አመቱ ለዲያብሎስ” ብለው ጽፈው ሰጡት። መጻፍስ የለም ይሁንብን ማለታቸውን ለመናገር ነው እንጂ እሱ በሁለት ዕብነ ሩካም ጽፎ አንዱን በሲዖል፣ አንዱን በዮርዳኖስ ጥሎታል። በዮርዳኖስ የጣለውን ጌታ ሲጠመቅ እንደ ሰውነቱ ረግጦ፣ እንድ አምላክነቱ አቅልጦ አጥፍቶታል። በሲዖል የጣለውን በዕለተ ዓርብ በአካለ ነፍስ ወርዶ ነፍሳትን ሲያወጣ አጥፍቶላቸዋል።  በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንን በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፤ እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል። (ቆላ. ፪፥፲፬) ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምም “ወሰጠጠ መጽሐፈ ዕዳሆሞ፤ የዕዳ ደብዳቤያቸውን ቀደደ” (ሰኞ ውዳሴ ማርያም)።   ነቢየ እግዚአብሔር  ኤርምያስ ስለ ዕዳ መጽሐፍ ሲናገር “የይሁዳ ኃጢአት በብረት ብርዕ በደንጊያ ሰሌዳ ተጽፎአል።” ይላል (ኤር. ፲፯፥፩)

ለምን በውኃ ተጠመቀ?

. ትንቢቱን ለመፈጸም፡

ሀ. “ጥሩ ውኃንም እረጫባችኋለሁ፤ እናንተም ከርኵሰታችሁ ትነፃላችሁ”  ጥሩ ውኃ የተባለ የጥምቀት ውኃ ነው፡፡ (ሕዝ. ፴፮፥፳፭)

ለ. “አቤቱ ውኖች አዩህ፤ ውሆችም አይተውህ ፈሩ” (መዝ. ፸፮፥፲፮)

ሐ.  “ድሆችና ምስኪኖች ውኃ ይሻሉ”  (ኢሳ. ፵፩፥፲፯)

መ. “ወይቤ ኩሎሙ እለ ጸምዑ ይሑር ኀበ ማይ፤ እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ ወደ ውኃ ኑ” (ኢሳ. ፶፭፥፩)

፪ኛ. ምሳሌው ለመመሰል፡

“ለታውጽእ ባሕር ኮሎ ዘይትሐውስ ዘቦ መንፈሰ ሕይወት” ባለ ጊዜ በልብ የሚሳቡ፣ በእግር የሚሽከረከሩ፣ በደመ ነፍስ ሕያዋን ሁነው የሚኖሩ ፍጥረታት ተገኝተዋል። በረው የሄዱ አሉ፣ የኢጥሙቃን፤ በዚያው የቀሩ የጥሙቃን ምሳሌ ነው። (ዘፍ. ፩፥፳፣ አክሲማሮስ ዘሐሙስ) አንድም በልብ የሚሳቡ የሰብእ ዓለም፣ በእግር የሚሽከረከሩ ከትሩፋት ወደ ትሩፋት የሚሄዱ የባሕታዊያን፣ በክንፍ የሚበሩ ተመስጦ ያላቸው የሰማዕታት ምሳሌ ነው።

፫ኛ. ፍጻሜውና ምሥጢሩ፦

  • ውኃ በዙፋን ካለ ንጉሥ በአደባባይ እስካለ ጽኑስ ለሁሉ ተመሳሳይ ነው። የጥምቀት መሠረቱ ለሁሉ ነውና፣
  • ውኃ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ይፈሳል። ጥምቀትም ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይደረጋልና፣
  • ውኃ ያነጻል፤ ጥምቀትም ያነጻናል።
  • ውኃ የወሰደው ፍለጋ የለውም። በጥምቀት የተሰረየ  ኃጢአት በፍዳ አይመረመርም፣
  • ውኃ መልክ ያሳያል፣ ያለመልማል። ጥምቀትም መልክአ ነፍስ ያሳያልና መልክአ ነፍስ ያለመልማል፡፡

፬ኛ. ውኃ ቀድሞ ሰብአ ትካትን በኋላ ግብፃውያንን አጥፍቶ ስለነበር ለመዓት እንጂ ለምሕረት አልተፈጠረም ብለው ስለነበር ለምሕረትም እንደተፈጠረ ለመጠየቅ ጥምቀቱን በውኃ አድርጓል። (ትርጓሜ ወንጌል፤ ማቴ. ፫፥፲፯)

ለምን በ ፴ ዘመኑ ተጠመቀ?

  • ሰው ሁሉ በ፴ ዘመኑ ሕገ ነፍስን ይሠራል፤ ቅስና እና ምንኩስናም በ፴ ዘመን ይገባል ሲል ነው፡፡(ዘፀ. ፬፥፫፤፩ኛዜና ፳፫፥፬፤ ፩ኛጢሞ. ፫፥፮-፲)
  •  አዳምን የ፴ ዘመን ጎልማሳ አድርጎ ፈጥሮት የሰጠውን ልጅነት አስወስዶ ነበርና የአዳምን ልጅነት ለመመለስ በ፴ ዘመኑ ተጠመቀ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን በማን ስም አጠመቀው?

ጌታችን ዮሐንስን አጥምቀኝ ባለው ጊዜ “ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ አንተን በማን ስም ላጥምቅህ? በአብ ስም እንዳላጠምቅህ አብ አባትህ በአንተ ሕልው ነው፣ በወልድ ስም እንዳላጠምቅህ ወልድ አንተ ነህ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንዳላጠምቅህ መንፈስ ቅዱስ ሕይወትህ በአንተ ሕልው ነው፤ ታዲያ በማን ስም ላጥምቅህ?” ብሎ ቢጠይቀው ጌታም ፦ “ወልዱ ለብሩክ ከሳቴ ብርሃን ተሣህለነ፤ አንተ ካህኑ ለዓለም በከመ ሲመቱ ለመልከ ጼዴቅ፤ እንደ መልከ ጼዴቅ ሥርዓት አንተ የዓለም ካህን ብርሃንን የምትገልጥ የአብ የባሕርይ ልጅ ሆይ ይቅር በለን”ብለህ አጥምቀኝ አለው፡፡ (ትርጓሜ ወንጌል ዘማቴ. ፫፥፲፮)

የጥምቀት አስፈላጊነት እና ጥቅም

. ለድኅነት (ለሥርየተ ኃጢአት)

አንድ ሰው መንፈሳዊ ልደትን የሚያገኘው በጥምቀት እና በእምነት ነው። ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ልደትን ለመግኘት የግድ መጠመቅ አለባቸው። ያለ ጥምቀት ክርስትና የለም። ጥምቀት አዲስ ሕይወትን የሚያስጥና ክርስቲያናዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ነው። ጌታችን  “ያመነ የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል።” (ማር. ፲፮፥፲፮) በማለት ጥምቀት ለመዳን የግድ አስፈላጊ መሆኑን አረጋግጦልናል። ቅዱስ ጳውሎስም ጥምቀት ለመዳን አስፈላጊ መሆኑን ሲገልጽ “እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፥ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለ ነበረው ሥራ አይደለም።” (ቲቶ ፫፥) ይላል።

ቅዱስ ጴጥሮስ ለመዳን አስፈላጊ የሆነውን ጥምቀት ምሳሌውን ተርጉሞ ሲናገር “ ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ፥ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኅ ዘመን በዘገየ ጊዜ ቀድሞ ክደውት ለነበሩት ሰበከላቸው፤ አሁንም እኛን በዚያው አምሳል በጥምቀት   ያድነናል፥ ሥጋን በዕድፍ በታመጠብ አይደለም፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ በመነሣቱ በእግዚአብሔርን መልካም ግብርን ያስተምር ዘንድ ነው እንጂ፡፡ (፩ኛጴጥ. ፫፥፳-፳፩) በማለት ጥምቀት የሰውነትን እድፍ ማስወገድ ሳይሆን ውስጣዊ እድፍን (ኃጢአትን) ማስወገጃ ምሥጢር መሆኑን ይመሰክራል።

ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፦ “ንስሓ ግቡ፥ ሁላችሁም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ ኃጢአታችሁም ይሰረይላችኋል፡፡ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ።” (ሐዋ. ፪፥፴፰)  ቅዱስ ጴጥሮስ ያስተማራቸውን አይሁድ የዘለዓለም ሕይወትን እንዲወርሱ ማድረግ ያለባቸውን ሲናገር መጠመቅ እንዳለባቸው አረጋግጧል።

. ለዳግም ልደት

አንድ ሰው በሥጋው ከእናት እና አባቱ እንደሚወለድ ከመንፈስ ቅዱስም በጥምቀት አማካኝነት መንፈሳዊ ልደትን ይወለዳል። “ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።” (ዮሐ. ፫፥፭) በጥምቀት የሚገኘው ልጅነት የማይጠፋ እና ዘለዓለማዊ የልጅነት ማረጋገጫ ነው። “ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም፥ በሕያውና ለዘለዓለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ።” (፩ኛ የጴጥ. ፩፥፳፫)

በጥምቀት የምናገኘው የልጅነት ጸጋ የመንግሥቱ ወራሾች ያደርገናል።ልጆችም ስለ ሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮኽ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ። ለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ።” (ገላ. ፬፥፮-፯) ጥምቀት ከዲያብሎስ ባርነት ወጥተን የእግዚአብሔርን ልጅነት የምናገኝበት፣ የመንግሥቱ ወርሽ የምንሆንበት ምሥጢር ነው።

. ከክርስቶስ ጋር አንድ መሆን

ጥምቀት የጌታችንን ሞቱን እና ትንሣኤውን ማመናችንን በተግባር የምንመሰክርበት እና ከሞቱ እና ከትንሣኤው የምንሳተፍበት ምሥጢር ነው።  ስንጠመቅ ወደ ውኃ ውስጥ መግባታችን የሞቱና የመቀበሩ ምሳሌ ነው። መውጣታችን ደግሞ የመነሣቱ ምሳሌ ነው። “ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠመቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደ ተጠመቅን አታውቁምን? እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፥ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን። ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን።” እንዲል (ሮሜ ፮፥ ፫)   

ከውኃ ውስጥ ሦስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ ማለቱ ጌታ በመቃብር ውስጥ ሦስት ቀን እና ሌሊት መቆየቱን ያስረዳል። በሦስተኛው ከውኃ መውጣቱ ጌታ በሦስተኛው ቀን ከመቃብር ለመውጣቱ ማስረጃ ነው። ክርስቲያኖች ከክርስቶስ ጋር እንነሣለን። በመጀመሪያ የነፍስ ትንሣኤን እናገኛለን። በመጨረሻ ደግሞ ነፍስና ሥጋቸን ተዋሕደው እንነሣለን። የነፍስ ትንሣኤ የተባለው በእምነትና በጥምቀት የምናገኘው ትንሣኤ ሲሆን በነፍስ ገነት መግባትን ያመለክታል። (ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት ገጽ ፪፻፵፯)።

. ክርስቶስን ለመልበስ

አሮጌውን አዳማዊ ሰውነታችንን አስወግደን “አዲስ ሰው” የተባለ ዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስን የምንለብሰው በጥምቀት ነው። ጥምቀት ለሕይወት የሆነ አዲስ ሰውነትን ገንዘብ የምናደርግበት ምሥጢር ነው። “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና።” (ገላ. ፫፥፳፯) ያልተጠመቀ ሰው ማንም ቢሆን ክርስቶስን ሊለብስ እና አዲስ ተፈጥሮን ገንዘብ ማድረግ አይችልም። “እርስ በርሳችሁ ውሸት አትነጋገሩ፥ አሮጌውን ሰው ከሥራው ጋር ገፋችሁታልና። የፈጠረውንም ምሳሌ እንዲመስል ዕውቀትን ለማግኘት የሚታደሰውን አዲሱን ሰው ለብሳችሁታል።” (ቆላ. ፫፥፱-፲)

. መንግ ሰማያትን ለመውረስ

ጥምቀት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርስበት ነው። እግዚአብሔር የሰጠንን ጸጋ ለመቀበል በጥምቀት የእግዚአብሔር ልጆች ሆነን ካልተወለድን በስተቀር ከእናት ከአባት በተወለድነው ተፈጥሯዊና ሥጋዊ ልደት መንፈሳዊ እና ሰማያዊ የሆነውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ አንችልም። “ኢየሱስም መልሶ፦ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም” (ዮሐ. ፫፥፭) አለው።  ጥምቀት አዲስ ልደት ተብሏል። “እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፥ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለ ነበረው ሥራ አይደለም” (ቲቶ ፫፥፭)

. የቤተ ክርስቲያን አባል ለመሆን

በኦሪተ የተገረዙ ሁሉ የእግዚአብሔር ወገንነትን መብት እንደሚያገኝ ሁሉ በጥምቀት የቤተ ክርስቲያን አባልነት መብት እናገኛለን። ምክኛቱም ግዝረት በጥምቀት ተተክቷልና።

“የሥጋንም ሰውነት በመገፈፍ፥ በክርስቶስ መገረዝ፥ በእጅ ባልተደረገ መገረዝ በእርሱ ሆናችሁ ደግሞ ተገረዛችሁ፤ በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችሁ፥ በጥምቀት ደግሞ፥ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር አሠራር በማመናችሁ፥ ከእርሱ ጋር ተነሣችሁ። እናንተም በበደላችሁና ሥጋችሁን ባለመገረዝ ሙታን በሆናችሁ ጊዜ፥ ከእርሱ ጋር ሕይወትን ሰጣችሁ፤ በደላችሁን ሁሉ ይቅር አላችሁ፤ በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፤ እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል።” (ቆላ. ፫፥፲፩-፲፫)

የጥምቀት ምሳሌ በብሉይ ኪዳን

፩. አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ከመልከ ጼዴቅ ጋር መገናኘቱ፦ አበ ብዙኃን አብርሃም ለአምስቱ ነገሥተ ሰዶም ረድቶ አራቱን ኮሎዶጎሞርን ድል ነሥቶ ሲመለስ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ሲሔድ መልከ ጼዴቅ ኅብስተ በረከት ጽዋዓ አኮቴት ይዞ ተቀብሎታል። አብርሃም፦ የምእመናን፣ ዮርዳኖስ፦ የጥምቀት፣ መልከ ጼዴቅ፦ የቀሳውስት፣ ኅብስተ በረከት ጽዋ አኮቴት፦ የሥጋው የደሙ ምሳሌ ነው።

፪ ኢዮብ ከዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ከደዌው ድኗል። ኢዮብ፦ የአዳም፣ ደዌ፦ የመርገመ ሥጋ የመርገመ ነፍስ፣ ዮርዳኖስ ፦ የጥምቀት ምሳሌ ነው።

፫. እስራኤል ዮርዳኖስን ተሻግረው ምድረ ርስት እንደገቡትም እመናንም አምነው ተጠምቀው ገነት መንግሥተ ሰማያት ለመግባታችን ምሳሌ ነው።

፬. ንዕማን በዮርዳኖስ ተጠምቆ ከደዌው ተፈውሷል። ንዕማን፦ የአዳም፣ ደዌ፦ የመርገመ ሥጋ፣ የመርገመ ነፍስ፣ ዮርዳኖስ፦ የጥምቀት ምሳሌ ነው።

የጥምቀት ዓይነቶች

ጥምቀት ከሦስት ወገን ነው።

፩ኛ. መዝገበ ውሉድ ፍቁራን የምትባል የጌታ ጥምቀት

፪ኛ. ጥምቀተ ዮሐንስ

፫ኛ. ጥምቀተ አይሁድ ናቸው።

ጥምቀተ አይሁድ እና ጥምቀተ ዮሐንስ አንድ አይሆንም ሁሉም ልጅነት አያሰጥም ቢሉ አንድ አይደሉም፤ ከሰውነታቸው ሰውነቱ እንዲበልጥ ከጥምቀታቸውም ጥምቀቱ ይበልጣል። አንድም ጥምቀት ከስምንት ወገን ነው። አራቱ ምሳሌያዊ አራቱ አማናዊ ናቸው።

ምሳሌያዊ የሚባሉት

፩ኛ. አጥመቃ ለምድር በማየ አይህ፤ ምድር በማየ ዐይህ መጠመቅ

፪ኛ. ወለኩሎሙ አበዊነ አጥመቆሙ ሙሴ በደመና፤  “ወንድሞች ሆይ፥ ይህን ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ። አባቶቻችን ሁሉ ከደመና በታች ነበሩ ሁሉም በባሕር መካከል ተሻገሩ፤ ሁሉም ሙሴን ይተባበሩ ዘንድ በደመናና በባሕር ተጠመቁ።” (፩ኛቆሮ. ፲፥፩-፪)

፫ኛ. ወተጠምቃ እገሪሆሙ ለካህናት፤ የካህናት እግሮቻቸው የዮርዳኖስን ውኃ በመርገጣቸው እንደ ጥምቀት ሆናቸው። (ኢያ. ፫፥፲፮)

፬ኛ. ጥምቀት ዮሐንስ፦ ዮሐንስ መጥምቁ ሲያጠምቃት የነበረችው ጥምቀት ናት። ዮሐንስ ለንስሓ በውኃ ብቻ እንጂ በመንፈስ ቅዱስ ስላላጠመቀ የዮሐንስ ጥምቀት የንስሓ እንጂ አማናዊ አልነበረችም።

 አማናዊ ጥምቀት

፩ኛ. መዝገበ ውሉድ ምቁራን የምትባል የጌታ ጥምቀት፦ በ፵ በ፹ ቀን ከውኃ እና ከመንፈስ የምንወለድባት አማናዊቷ ጥምቀት ነች።

. አንብዓ ንስሓ፦ ማለት በንስሓ ጊዜ የሚፈሰው የለቅሶ፣ የሐዘን ዕንባ ነው። የንስሓ ዕንባ ሥርየተ ኃጢአትን ስለሚያሰጥ እንደ ጥምቀት ይቆጠራል። (ድርሳነ ጎርጎርዮስ ፴፱፥፲)

. ደመ ሰማዕት፦ ደምን በማፍሰስ የምትፈጸም ጥምቀት ናት። ይህች ጥምቀት ክርስቶስን መምሰል የምታሰጥ እጅግ የከበረች ጥምቀት ናት፤ ዋጋዋም ከፍ ያለ ነው።

4. ባሕረ እሳት፡- እንደ ደመ ሰማዕታት በእሳት ባሕር ተጠምቆ ድኅነትን መግኘት ነው።

ጥምቀት ስንት ጊዜ ትፈጸማለች?

በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ የምትፈጸም ጥምቀት አንዲት ናት ። አንድ ጊዜ ከተፈጸመች  (ከተሰጠች) አትደገምም። ከቤተ ክርስቲያን የማይደገሙ ምሥጢራት መካከል አንዷ ነች። በካህን፣ በኢጲስ ቆጶስ እጅ የምትፈጸም ጥምቀት አንዲት ነች ። “ሊቀ ጳጳስ ወይም ኢጲስ ቆጶስ ሳይመጣ አናጠምቅም አይበሉ፤ የማጥመቅ ሥልጣን ያለው ያጥምቅ እንጂ፣ የጥምቀት ሥልጣን አንዲት ናት ።” (ፍትሃ ነገሥት አንቀጽ ፫፥፳፱)። አማናዊቱ ጥምቀት አንዲት ናት ። “አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖት፣ አንዲት ጥምቀት።” (ኤፌ. ፬፥፭)

ለምን በየዓመቱ ይከበራል?

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የጥምቀት በዓልን የምታከበረው የጌታችን የማዳኑን ምሥጢር ለማዘከርና  ለመመስከርም ነው፡፡ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ “የጠበሉን መረጨት አይተው  በቀድሞ ዘመን ወደ ሀገራችን መጥተው የነበሩ ኢየሱሳውያን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን  በየዓመቱ ታጠምቃለች” ያሉትን መልስ ሲሰጡ “ይህን ምትፈጽመው ጌታችን ለእኛ ብሎ ያሳየውን ትሕትና ለመመስከር እና  ለምእመናን የጌታችን በረከተ ጥምቀት ለማሳተፍ እንጂ የተጠመቁትን ምእመናን  እየመለሰች በየዓመቱ አታጠምቅም” ብለዋል፡፡(የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ገጽ ፻፳፫)። ስለዚህ የጥምቀትን በዓል በየዓመቱ የምናከብረው ጌታችን ለኛ ያደረገውን የድኅነት መንገድ ለማሰብ፣ ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነጻ የወጣንበትን ምሥጢር ለመዘከር፣ ጌታችን ከገሊላ ወደ ዮሐንስ ያደረገውን ጉዞ ለማሰብ፣ ከበዓለ ጥምቀቱ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን ለማግኘት ነው።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ከተራ

እንኳን አደረሳችሁ፣ አደረሰን!

ከተራ፦ ከተረ ከበበ ካለው የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ ፍችው ውኃ መከተር፣ መገደብ ማለት ነው፡፡ የጥምቀት ዋዜማ ታቦተ ሕጉ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ውኃ ባለበት አካባቢ ስለሚያድር የየአጥቢያው ሕዝብ እየተሰበሰበ በወንዝ ዳር ወይም በምንጭ አካባቢ ድንኳን ይተከላል፡፡ ድንኳንም ከሌለ ዳስ ሲጥል ይውላል፡፡ የምንጮች ውኃም ጉድጓድ እየተቆፈረ ውኃው እንዳይፈስ እንዲጠራቀም ይከተራል፡፡

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን “ከተራ” በመባል የሚታወቀው የጥምቀት ዋዜማው ነው። ሠርግው ሀብለ ሥላሴ (፲፲፻፹፩፤ ገጽ ፰) ብለው ሲፈቱት፣ ደስታ ተክለ ወልድ ደግሞ በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው (፲፱፻፷፩፤ ፮፺፬) የጥምቀት ዋዜማ፣ ጥር ፲ የሚከበር የጠራ፣ ንጹሕ ወራጅ ውኃ የሚከተርበት፣ ታቦታትና ምእመናን ወደ ወንዝ የሚወርዱበት ጊዜ” ነው በማለት ይፈቱታል፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም (፲፱፻፵፰፤ ገጽ ፭፻፶፭) ከተረ የሚለውን ቃል በቁሙ፣ “ዘጋ፣ አቆመ፣ አገደ፣ ከለከለ፡፡” ማለት ነው ብለው ይፈቱታል፡፡

በየዓመቱ ጥር ፲ ቀን የምእመናኑ አብዛኛው ሥራ ውኃውን መከተርና መገደብ በመሆኑ ዕለቱ ከተራ የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ውኃው የሚከተረው በማግስቱ ጥር ፲፩ ቀን የጥምቀት በዓል ስለሚከበር  ለሕዝቡ መጠመቂያ  እንዲሆን ነው፡፡ በየሰበካው ቦታ ተለይቶና ተከልሎ ታቦታቱ በዳስ ወይም በድንኳን የሚያድሩበት፣ የተለያዩ የውኃ አካላት ተጠርገው የሚከተሩበት ወይም ሰው ሠራሽ የግድብ ውኃ የሚበጅበት ስፍራ “ባሕረ ጥምቀት፣ የታቦት ማደርያ” እየተባለ ይጠራል።  

በዓሉ የሚከበርበትን ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ዳራ

የበዓለ ጥምቀት አከባበር በኢትዮጵያ የተጀመረው የክርስትና እምነት እንደገባ መሆኑ ቢታመንም እስከ ስድስተኛው መ/ክ/ዘመን ድረስ አሁን በምናከብርበት ሁኔታ የሚታሰብበት ሥርዓት አልነበረም። ጥምቀትን በሜዳ እና በውኃ አካላት ማክበር የተጀመረው በዘመነ ዐፄ ገብረ መስቀል (፭፻፴-፭፻፵፬ ዓ.ም ) ሲሆን የቅዱስ ያሬድ (፭፻፭-፭፻፸፪ ዓ.ም) ዜማ መስፋፋት ጋር ተያይዞ ታቦታቱ በየዓመቱ ጥር ፲፩ ቀን ጠዋት ወደ ወንዝ ወርደው ማታ ይመለሱ ነበር። (ሐመር መጽሄት ጥር/የካቲት ፲፱፻፺፷ ዓ.ም ገጽ ፮)

ከዚህም በተጨማሪ በቅዱስ ላልይበላ ዘመነ መንግሥት በኢትዮጵያ ምድር እየተመላለሱ በብሕትውና እና በስብከተ ወንጌል ያገለግሉ የነበሩት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በአክሱም፣ በመቐለና በመርጡለ ማርያም እየተዘዋወሩ ባሕረ ጥምቀቱን ባርከዋል፡፡ በዐፄ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት (፩፪፻፷-፲፪፻፸፭ ዓ.ም) በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት (፲፪፻፫ ዓ.ም) አሳሳቢነት የተጀመረው ሥርዐተ በዓል ተጠናክሮ እንዲቀጥል በዐዋጅ ትእዛዝ አስተላልፈዋል፡፡ ታቦታቱም በሕዝብ ጥበቃና ክብካቤ ተደርጎላቸው በየጥምቀተ ባሕሩ እንዲያድሩ ወስነዋል፡፡ የበዓሉ አከባበር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋና አድማሱ ብሔራዊነትን እየያዘ መጣ፡፡

ከዐፄ ገብረ መስቀል ጀምሮ የአደባባይ በዓል የሆነው የጥምቀት በዓል በ፲፭ኛው ክ/ዘመን በደገኛው ኢትዮጵያዊው ንጉሠ ነገሥት ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ(፲፬፻፳፮-፲፬፻፷ ዓ.ም) አማካኝነት ታቦታቱ ወደ ወንዝ ወርደው ዕለቱን እንዳይመለሱ፣ በዚያ ፈንታ በጥምቀት ዋዜማ ጥር ፲ ቀን ከሰዓት በኋላ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ ወርደው እንዲያድሩ፣ ሀገሩንም በኪደተ እግር ይባርኩም ዘንድ በሄዱበት መንገድ እንዳይመለሱ በዐዋጅ ወሰኑ፡፡ ይህን ታሪክ በመከተል ዐፄ ናዖድ (፲፬፻፹፮-፲፭፻) ዓ.ም) ማንኛውም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ምእመን ታቦተ ሕጉ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ በሚወርድበት እና ከባሕረ ጥምቀቱ ወደ ቤተ መቅደሱ በሚመለስበት ጊዜ አጅቦ አውርዶ፣ አጅቦ መመለስ እንዳለበት በዐዋጅ አስነግረው ነበር፡፡ ሕዝቡም ታቦታተ ሕጉን በሆታና በእልልታ ከቤተ መቅደስ አጅቦ ከአወጣ በኋላ በባሕረ ጥምቀት ከትሞ ማደር ተጀመረ። ( ሐመር መጽሔት ጥር/የካቲት 1998 ዓ.ም)

ታቦታት ከአንድ በላይ ሆነው ወደ ከተራው ስለሚሄዱ እግዚአብሔር አምላክ ለነብዩ ሙሴ “የታቦት መኖር ከእናንተ ጋር የመኖሬ ምልክት ነው” (ዘፀ. ፳፭÷፩) እንዳለው ታቦተ ሕጉን ተሸክመው ዮርዳኖስን እንደ ተሻገሩት ካህናተ ኦሪት፤ ካህናቱ ታቦተ ሕጉን በራሳቸው ተሸክመው የብሉዩን ሥርዓት ከሐዲስ ኪዳን ጋር አንድ አድርገው የሐዲስ ኪዳን መሠረት ኢየሱስ ክርስቶስን እያሰቡ ወደ ከተራ (ዮርዳኖስ) ይጓዛሉ፡፡

የከተራ በዓል ምሳሌያት

በበዓለ ጥምቀት ዋዜማ የታቦታቱ ወደ ወንዝ መውረድና የባሕረ ጥምቀቱ መዘጋጀት ሃይማኖታዊ ታሪክና ምሳሌ አለው፡፡ የቃል ኪዳኑን ታቦት አክብሮ መጓዝና ወደ ወንዝ መወረድ የተጀመረው በአሮን ልጅ በአልዓዛር ጊዜ ነው፡፡ ኢያሱ በሙሴ እግር ተተክቶ ሕዝበ እስራኤልን እየመራ ከዮርዳኖስ ወንዝ ሲደርስ ባሕሩ ከሁለት ይከፈልና ወራጁም ይቆም (ይከተር) ነበር፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ወደ ምድረ ርስት ለመግባት የዮርዳኖስን ወንዝ ሲሻገሩ፡- ድንኳን ጥለው የቃል ኪዳኑን ታቦት በድንኳን ውስጥ አድርገው ሌዋውያኑ በዙሪያው፣ ካህናቱ ደግሞ በውስጥ ኾነው እግዚአብሔርን እያመሰገኑ አድረው በማለዳ ተሻግረዋል (ኢያ. ፫÷፰-፱)፡፡ ካህናቱ የቃል ኪዳኑን ታቦት አክብረው የወንዙን ዳርቻ በረገጡት ጊዜ እንደ ክረምት ማዕበል ይወርድ የነበረው ውኃ ግራና ቀኝ ተከፍሎ እንደ ግድግዳ ወደ ላይ ቆሟል፡፡ ሕዝቡ ተሻግሮ እስከሚያበቃ ታቦተ ጽዮንን ያከበሩት ካህናት ከወንዙ መሐል ይቆሙ ነበር፡፡ በዚህ መሠረት “ወተጠምቃ እገሪሆሙ ለካህናት፤ የካህናት እግሮቻቸው የዮርዳኖስን ውኃ በመርገጣቸው እንደ ጥምቀት ሆናቸው” እንዲል በሐዲስ ኪዳነ ጌታችን ለመሠረተው ሥርዐተ ጥምቀት ምሳሌ ነበር፡

ቤተ ክርስቲያናችን የጥምቀትን ዋዜማ ከተራ ብላ የጠራችው ከዚህ በመነሣት ነው፡፡ ጌታችን በተጠመቀ ጊዜ የዮርዳኖስ ወንዝ የላይኛው ሸሽቶ ወደ ላይ ተመልሶ ሽቅብ ፈሷል፡፡ የታቹም ወደ ታች ሸሽቷል፡፡ የላይኛው ፈሳሽ ተቋርጦ እንደ ክምር ተቆልሎ ቀርቷል። ቅዱስ ዳዊት የተመለከተውም ይህንኑ ነው። ከአዳም ጀምሮ እስከ ክርስቶስ ድረስ በዘር ይወርድ የነበረው ፍዳ መርገም በክርስቶስ ቤዛነት ተቋርጦ፤ የታቹም ፈጽሞ መድረቁ ኃጢአተ አዳም የመጥፋቱ ምሳሌ ነው፡፡

እስራኤል ፈለገ ዮርዳኖስን ተሻግረው ወደ ኢያሪኮ መሔዳቸው ምእመናን በጥምቀት ከኃጢአት ቍራኝነት ተላቀው እግራቸውን ወደ ልምላሜ ገነት ወደ ዕረፍት መንግሥተ ሰማያት አቅንተው ለመሔዳቸው ምሳሌ ነው፡፡ ኢያሱ የጌታ፣ እስራኤል የምእመናን፣ ዮርዳኖስ የጥምቀት፣ ምድረ ርስት የገነት መንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ ታቦቱን አክብሮ የሚሔደው ካህን የቅዱስ ዮሐንስ፣ ታቦቱ የጌታችን፣ ባሕረ ጥምቀቱ የዮርዳኖስ ወንዝ፣ ታቦታቱን አጅበው የሚሔዱትና በዓሉን የሚያከብሩት ምእመናን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ እየመጡ የንስሓ ጥምቀት ሲጠመቁ የነበሩት ሰዎች ምሳሌዎች ናቸው፡፡

ታቦታቱ በጥምቀት ዋዜማ ከመንበራቸው ወደ ጥምቀተ ባሕር መውረዳቸውና በዚያ ማደራቸው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ ከማታው ጀምሮ መውረዱንና ተሰልፎ ተራውን ሲጠብቅ ማደሩን ያጠይቃል፡፡ “ጥምቀት የሞቱና የትንሣኤው ምሳሌ ነው፡፡ ከኃጥአን ጋር ተቆጥሮ እንዲጠመቅና እንዲሰቀል የተጻፈውን ቃል ንስሓና ጥምቀት የማያስፈልገው ሲሆን ነገር ግን ፍጹም ኃጥእ መስሎ በዮሐንስ እጅ ጥምቀትን ለመፈጸም በማየ ዮርዳኖስ ተጠመቀ፡፡” (ኪ.ወ.ክ፤ ፭፲፯)፡፡

ጌታችን የተጠመቀበት ወርኀ ጥር በእስራኤላውያን ዘንድ የዝናብ፣ የበረዶ ወራት ነው፡፡ ከወንዝ ዳር ያለ መጠለያ መዋልና ማደር አይቻልም፡፡ በመሆኑም ከዮሐንስ ለመጠመቅ የሚሄዱ ሰዎች ሁሉ በዮርዳኖስ ዙሪያ ድንኳናቸውን ተክለው ያርፉ ነበር፡፡ በዚህ አንጻር ዛሬም በባሕረ ጥምቀት ዙሪያ ድንኳኖች ዳሶች ይጣላሉ፡፡ እኛ በዚህ ወቅት ታቦት ይዘን፣ ከወንዝ ወርደን፣ ድንኳን ተክለን በማክበራችን ይፈጸማል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ተወልደ ኢየሱስ በቤተ ልሔም ዘይሁዳ” (ቅዱስ ያሬድ)

ውድ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎቻችን እንኳን ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን!

በዲ/ን አብርሃም ባንቲሁን

የጌታችን ልደት በነገረ ድኅነት ትልቅ ስፍራ የያዘና እግዚአብሔር ሰው ሆኖ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ፍጹም ልዩ መሆኑን ያሳየ ነው። በጌታችን ልደት ቤተ ልሔም ሰማይን የመሰለችበት፣ መስተፃርራን የነበሩ ሰውና መላእክት በአንድነት ለምስጋና የታደሙበት ነው። የእረኞች አንደበት ከመላእክት ጋር ለሰማያዊ ምስጋና ብቁ የሆነበት፤ ግዕዛን የሌላቸው እንስሳት “ሠራኢ መጋቢያችን፣ በዘባነ ኪሩቤል በሰማያት የምትገለጥ አንተ ነህ” ሲሉ እስትንፋሳቸውን የገበሩለት ነገሥታት “በመንግሠትህ ሽረት በባሕርይህ ህልፈት የሌለብህ የነገሥታት ንጉሥ አንተ ነህ” ሲሉ ወርቅን ለመንግሥቱ፣ ዕጣንን ለክህነቱ፣ ከርቤን ለሕማሙ እጅ መንሻን ያበረከቱለት፤ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በግብረ መንፈስ ቅዱስ ተፀንሶ በፍጹም ድንግልና በከብቶች በረት ተወለደ፡፡  ይህ ልደት በእውነት ልዩ ነው።

ይህን የጌታችንን ልደት አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በአርጋኖን (ዘሰኑይ) ላይ እንዲህ ሲል በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ በአድናቆት ያመሰግናል “ለዚህ ልደት መስገድ መገዛት ይገባል፤ ክብር ምስጋና ለዚህ ልደት ይገባል፤ ጌትነትና ገናንነት፣ ኀያልነት፣ እልልታ፣ ግርግታ ለዚህ ልደት ይገባል፡፡ ይህ ጥበብ ፍልስፍና ዕፁብ ድንቅ ነው፡፡ ለዚህ አንክሮ ይገባል፤ ይህም የሥጋዊ ምሥጢር ምን ይረቅ? ምን ይጠልቅ? ለዚህ አንክሮ ይገባል፡፡ ይህም ሰው መሆን ሥጋ መልበስ እጅግ ዕፁብ ድንቅ ነው!” ይላል።

ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊም በረቡዕ ውዳሴ ማርያም በጌታ ልደት የተደረገልንን ድንቅ የማዳን ሥራ በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ ነበር ያለው፦ “በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ታላቅ ብርሃን ወጣላቸው፤ በቅዱሳን የሚያድር እግዚአብሔር እኛን ለማዳን ልዩ ከሆነች ድንግል ሰው ሆኗልና ኑ ይህን ድንቅ እዩ፣ ስለተገለጠልን ምሥጢር ምስጋና አቅርቡ፤ ሰው የማይሆን ሰው ሆኗልና፤ ቃል ተዋሕዷልና፤ ቅድምና የሌለው ሥጋ ቀዳማዊ ሆነ፣ ዘመን የማይቆጠርለት መለኮት ዘመን ተቆጠረለት።” በማለት ሲያደንቅ፡-  ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ደግሞ “ይህች ቤተ ልሔም መንግሥተ ሰማያትን መሰለች” በማለት የጌታ ልደት ልዩ መሆኑን ይገልጻል።

ቤተ ልሔም ማለት ቤተ ኅብስት፣ የእንጀራ ቤት ማለት ነው። ይህም ካሌብ እስራኤል ዘሥጋ ምድረ ርስት፣ ኢያሪኮን “ኃይል ዘእግዚአብሔር ኲናት ዘኢያሱ” ብለው በኢያሱ መስፍንነት ሲወርሱ ከኢያሱ የተሰጠችው ምድር፣ ኬብሮን ነበረች። ይህችም የይሁዳ ምድር በኋላም የቅዱስ ዳዊት ከተማ የሆነች ናት። አስቀድሞ ካሌብ ከብታ የምትባል ሚስት አግብቶ በሚስቱ ከብታ አላት፤ ትርጓሜውም የምስጋና ቤት ማለት ነው፤ ይህም ካሌብ በመንፈሰ እግዚአብሔር በዚህች ምድር የሚገለጠውን የክርስቶስ የልደቱን ነገር እና የመላእክትን ምስጋና ስለተረዳ ነበር። በኋላም ካሌብ ኤፍራታ የምትባል ሚስት አገባ ቦታዋን በዚህች ሚስቱ እንደገና ኤፍራታ ብሎ ጠራት። ኤፍራታ ማለት ፀዋሪተ ፍሬ፣ ፍሬ በውስጧ ያለባት ማለት ነው።

ይህችውም የእመቤታችን ምሳሌ ናት የሕይወት ፍሬ ክርስቶስን ወልዳልናለችና፤ “አንቲ ውእቱ ዕፅ ቡሩክ ዕፀ ሕይወት ዕፀ መድኃኒት ህየንተ ዕፀ ሕይወት ዘውስተ ገነት ዘኮንኪ ዕፀ ሕይወት በዲበምድር ፍሬኪኒ ፍሬ ሕይወት ውእቱ፤ አንቺ የተባረክሽ ዕፅ ነሽ፤ የሕይወትና የደኅንነት ዕፅ ነሽ፤ በገነት ውስጥ ባለው ዕፅ ሕይወት ፈንታ በዚህ ዓለም የሕይወት ዕፅ ሆንሽ፤ ፍሬሽም የሕይወት ፍሬ ነው ” እንዳለ ቅዱስ ያሬድ በአንቀጸ ብርሃን።

ቤተ ልሔም ይህን ስያሜዋን ያገኘችው ካሌብ ከኤፍራታ ባገኘው ልጁ በልሔም ነው፤ ልሔም ማለት ኅብስት፣ እንጀራ ማለት ነው፡፡ ይህም ምሳሌነቱ የጌታ ነው፤ ይኸውም አማናዊ፣ እውነተኛ የሕይወት እንጀራ፣ ኅብስተ ሕይወት ክርስቶስ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ ሊያድነን በቤተ ልሔም እውነተኛ እንጀራ ሆኖ ተወልዶልናልና ነው። “ከሰማይ የወረደ ሕያው እንጀራ እኔ ነኝ፤ ሰው ከዚህ እንጀራ ቢበላ ለዘለዓለም ይኖራል፤ እኔም ስለ ዓለም ሕይወት የምሰጠው እንጀራ ሥጋዬ ነው።” እንዲል (ዮሐ. ፮፥፶፩)።

በክርስቶስ ልደት መላእክት ባልተለመደ ሁኔታ ከሰዎች ጋር ተባብረው “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ፤ በሰማያት ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ሰላምም ለሰው ልጅ በምድር እርሱ በሚፈቅደው” እያሉ ንጉሥ ክርስቶስን አመሰገኑ። (ሉቃ. ፪፥፲፬) በሰማያት በዘባነ ኪሩቤል የሚገለጥ፤ ፍጹማን ግሩማን በሚሆኑ መላእክት፣ ሊቃነ መላእክት፣ ሥልጣናት፣ አጋእዝት የሚመሰገን ሰማያዊው ንጉሥ ዛሬ ስለ እኛ ፍቅር ሲል ሊነገር በማይችል ፍጹም ትሕትና እንደ ሕፃናት ተወለደ፣ በእናቱ እቅፍ ሆኖ ከኃጢአት በቀር የእኛን ባሕርይ ባሕርዩ አድርጎ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው ሆኗልና።

”ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኀያል አምላክ፥ የዘለዓለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል።” (ኢሳ. ፱፥፮) ተብሎ እንደተጻፈ።

ለዚህ ለክርስቶስ ፍቅር አንክሮ ይገባል፤ በሙሉ አፍአዊና ውሳጣዊ ኅሊናችን እርሱን ዘወትር እናመስግን። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ዻውሎስ ይህን ፍጹም ፍቅር ለሰው ልጅ በኃጢኣት ተዳድፈን ለነበርን መደረጉን እያሰበ በአንክሮ “ታስበው ዘንድ ሰው ምንድር ነው? ወይስ ትጐበኘው ዘንድ የሰው ልጅ ምንድር ነው? ከመላእክት ይልቅ በጥቂት አሳነስኸው፤ የክብርና የምስጋና ዘውድ ጫንህለት፥ በእጆችህም ሥራ ላይ ሾምኸው፤ ሁሉን ከእግሮቹ በታች አስገዛህለት” (ዕብ. ፪፥፮) በማለት ይናገራል። እኛም በክርስቶስ የተጠራን ሁላችን ይህን የአምላክ ፍቅር ዘወትር በልቡናችን እንድንሥልና ከሰው ጋር ሁሉ በትሕትናና በፍቅር እንድንኖር ይመክረናል፡፡

“እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፥ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ፤ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለች ይህች ሐሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ትኑር፤ እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከሰው ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ አልቆጠረም ነገር ግን፥ የባሪያውን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ” (ፊል. ፪፥፭) ይለናል ።

ይህ የጌታ ልደት የቤተ ክርስቲያን አንድነት ነው። ሁሉ በአንድነት የተሰባሰቡበት በጋራ የዘመሩበት፤ በዚህች በበረት፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምሳሌ በሆነችው ጌታችን ከመሐል ከእናቱ ጋር እንዲሁም አረጋዊ ዮሴፍ ከማኅበረ ጻድቃን፣ ሰማያውያን መላእክት፣ እረኞች፣ ሰብአ ሰገል፣ እንስሳትም ሳይቀሩ በአንድነት የተገኙባት የፍቅርና የአንድነት ቤት ናት። ስለዚህ እኛም የክርስቶስ አባግዓ መርዔቱ፣ የመንጋው በጎች፣ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በፍጹም አንድነት መኖር እንዳለብን ያሳስበናል፡፡

“ወንድሞች ሆይ፥ ሁላችሁ አንድ ንግግር እንድትናገሩ፤ በአንድ ልብና በአንድ ሐሳብም የተባበራችሁ እንድትሆኑ እንጂ መለያየት በመካከላችሁ እንዳይሆን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እለምናችኋለሁ።” (፩ኛቆሮ. ፩፥፲) በማለት ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ዻውሎስ ያስተምረናል።

ውድ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች፡- የጌታችን ልደት በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለምንኖር ለእኛ ታላቅ የብርሃን ቀን ነው። በዚህ የልደት ብርሃን ቀን እንደ ቤተ ልሔም እረኞች ከቤተሰባችሁ ርቃችሁ ትምህርታችሁን በመከታተል ላይ የምትገኙ ሲሆን በጌታችን ልደት ቀን አንድ በምታደረገን ቤተ ልሔም የተወለደው ንጉሥ ክርስቶስ ዕለት ዕለት የሚሰዋባት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደ እረኞቹና እንደ መላእክቱ ከሊቃውንቱና ከምእመናን ጋር በምስጋና ልታሳልፉ ይገባል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና አረጋዊ ዮሴፍ ለመቆጠር፤ ቅዱሳን መላእክት ለምስጋና፤ እረኞች የተወለደውን መድኃኒት ለማየት፤ የጥበብ ሰዎች (ሰብአ ሰገል) ቁሳዊና መንፈሳዊ ስጦታን ለመስጠት፤ የሄሮድስ ወታደሮች ለመሰለል በጌታ ልደት በቤተልሔም ተሰበሰቡ።

ሰብአ ሰገል ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤን ሊሰጡት ይዘውለት ሄዱ፤ እናንተስ ለጌታችን ልደት ምን ይዛችሁለት ልትሄዱ ምን ልትሰጡት አስባችሁ ይሆን?

ለእግዚአብሔርስ ምንም የምንሰጠው ነገር አይኖረንም፤ ከእርሱ ሁል ጊዜ እንቀበላለን እንጂ፤ እርሱማ ሁሉ የርሱ የሆነ፤ ሁሉን ለእኛ የሰጠን፣ የሚሰጠንም፡ አንድያ ልጁን እስከ መስጠት የወደደን፡ የሚሰጥ እንጂ የማይሰጡት አምላክ ነው። እርሱ  ከእኛ የሚፈልገው አንድ ስጦታ አለ። ይህ ስጦታ ምንድነው? ያልን እንደሆነ መልሱ ቅዱሳን አርሱን እንደመሰሉት እኛም እርሱን እንድመስል ነው። “እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እናንተም እኔን ምሰሉ።” እንዲል (፩ኛ ቆሮ. ፲፩፥፩)

እርሱ ራሱን ለኛ እንደሰጠን እኛም ራሳችንን ለእርሱ እንስጠው። ለመንግሥቱም የምንገባ እንሆን ዘንድ በብርሃኑ እንመላለስ፦ ንስሓ እንግባ፤ የሰጠንም እንቀበለው፤ ሥጋውን እንብላ ደሙንም እንጠጣ።

እርሱ የሰላም አለቃ እንደሆነ እኛም የሰላም ሰዎች ሰላማውያን እንሁን። እምነታችንን፣ ተስፋችንን፣ ፍቅራችንን አጽንተን እርሱን መስለን በብርሃኑ (በትሕትና፣ በበጎነት፣…) እንመላለስ፤ መለያየትን ከእኛ እናርቅ የዚያን ጊዜ ከመላእክት ጋር ደስ እያለን፦ “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ፤ በሰማያት ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ሰላምም ለሰው ልጅ በምድር እርሱ በሚፈቅደው” (ሉቃ. ፪፥፲፬) እያልን እንዘምራለን። የጌታችንና የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱ በዓል በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን። አሜን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር። አሜን!

በዓለ ክብሩ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ ሠለስቱ ደቂቅን (አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል) ከነደደ እሳት ያዳነበትን መታሰቢያ በዓል በድምቀት ታከብራለች፡፡

ቅዱስ ገብርኤል አብሣሪ መልአክ እንደሆነ ሁሉ ምእመናን እግዚአብሔርን በማምለካቸው ምክንያት ከአላውያን ገዢዎች ከሚደርስባቸው መከራም የሚታደጋቸው መልአክ ነው፡፡ የፋርስ ንጉሥ የነበረው ናብከደነፆር እግዚአብሔር አምላክ ምድሪቱን እና ሕዝቡን ያስተዳድር ዘንድ ቢፈቅድለት በትዕቢት ተሞልቶ “በኃይሌ አደርጋለሁ፣ በማስተዋል ጥበቤም የአሕዛብን ድንበሮች አርቃለሁ፣ ሀብታቸውንም እዘርፋለሁ፣ የሚቀመጡባቸውንም ከተሞች አናውጣለሁ፣ በእጄም ዓለምን ሁሉ እንደ ወፍ ቤት እሰበስባለሁ፣ እንደ ተተወ እንቁላልም እወስዳቸዋለሁ፤ ከእኔም የሚያመልጥ የለም፤ የሚቃወመኝም የለም” ብሎ በመታበይ የወርቅ ጣዖትን አሠርቶ በባቢሎን አውራጃ ቁመቱ ስድሳ ክንድ፣ ወርዱም ስድስት ክንድ የሆነ የወርቅ ምስል አሠርቶ በዱራ ሜዳ ላይ አቆመው፡፡ (ኢሳ. ፲፥፲፫-፲፬፤ ዳን.፫፥፩)፡፡

መኳንንትንና ሹሞቹን እንዲሁም ሕዝቡን አስጠርቶ በዐዋጅ ነጋሪ “ንጉሡ ናቡከደነፆር ላቆመው ለወርቁ ምስል ስገዱ፤ ወድቆም የማይሰግድ በዚያን ጊዜ በሚነድ እሳት እቶን ውስጥ ይጣላል” ሲል ዐዋጅ አስነገረ፡፡ ይህን ዐዋጅ የሰሙ የንጉሥ ሹማምንት ሁሉ ተደፍተው ለወርቁ ምስል ሰገዱ፡፡ ነገር ግን በመካከላቸው አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል ንጉሡ ላቆመው ምስል አልሰገዱም፡፡

ነገር ሠሪዎችም ይህንን ወሬ ለንጉሥ ባደረሱ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ ካስጠራቸው በኋላ “… አምላኬን አለማምለካችሁ ላቆምሁትም ለወርቁ ምስል አለመስገዳችሁ እውነት ነውን?” ሲል ጠየቃቸው፡፡

አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል ግን በንጉሡ ፊት ቆመው “ንጉሥ ሆይ፥ እኛ የምናመልከው አምላክ በሰማይ አለ፡፡ ከሚነድደው ከእቶኑ እሳት ያድነን ዘንድ ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል፡፡ ንጉሥ ሆይ! ይህም ባይሆን አማልእክትህን እንዳናመልክ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንዳንሰግድ ዕወቅ” አሉት፡፡ (ዳን.፫፥፬፫-፲፰)፡፡

የንጉሥ ናቡከደነፆር ቁጣ ከፊት ይልቅ እጅግ ነደደ፤ እሳቱንም ሰባት እጥፍ እንዲያቀጣጥሉና እነዚህን ሦስት ብላቴኖች እጅና እግራቸውን አስረው ከእቶን እሳት ውስጥ እንዲጨምሩአቸው አዘዘ፤ ጋሻ ጃግሬዎቹም ፈጥነው ወደሚነደው እሳት ጨመሯቸው፡፡ እግዚአብሔርም የሦስቱን ወጣቶች የእምነት ጽናት ተመለከተ፡፡ በፊቱ የሚቆመውን ባለሟሉን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤልንም ከመጣባቸው መከራ ይታደጋቸው ዘንድ ላከላቸው፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ከእስራታቸው ፈታቸው፤ እሳቱንም እንደ ውኃ አቀዘቀዘው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅም ከተጣሉበት ሆነው መልአኩን ልኮ ከዚህ እቶን እሳት ያዳናቸውን አምላክ አመሰገኑት፡፡

ንጉሡ ናብከደነፆርም ሠለስቱ ደቂቅ እሳቱ አንዳች ጉዳት ሳያደርስባቸው በእሳት ውስጥ ሲመላለሱ ተመለከተ፡፡ “እነሆ እኔ የተፈቱ በእሳቱም መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎችን በዚያ አያለሁ ምንም የነካቸው የለም፤ የአራተኛውም መልክ የእግዚአብሔርን ልጅ ይመስላል” ብሎ ፊቱን ጸፍቶ አፉንም ከፍቶ እንዲናገር አደረገው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅ በእሳቱ ውስጥ ሆነው እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ሰማቸው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ከነደደው እሳት አዳናቸው፡፡ (ዳን. ፫፥፳፬-፳፮)

ናብከደነፆር የተደረገውን ተአምር ተመልክቶ ወደ እሳቱ በመቅረብ ለሦስቱ ብላቴኖች  “እናንተ የልዑል አምላክ ባሪያዎች ሲድራቅ፣ ሚሳቅንና አብደናጎም ኑ ውጡ” ብሎ ተናገራቸው፡፡ (ዳን.፫፥፳፮) እነርሱም እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ወጡ፡፡ መሳፍንቱና ሹማምቶችም የሚያመልኩት አምላካቸው ቅዱስ እግዚአብሔር የሚነደው እሳት ሰውነታቸውን ሳይበላ፣ የራሳቸውም ጸጉር ሳይነካ፣ የእሳቱም ሽታ በላያቸው እንዳልነበረ አዩ፡፡ ንጉሡ ናቡከደነፆርም በሠለስቱ ደቅቅ ፊት ለእግዚአብሔር ሰገደ፡፡ እግዚአብሔርንም እያመሰገነ ሕዝቡን ሁሉ የብላቴኖቹ ሠለስቱ ደቂቅን አምላክ እንዲያመልኩ፤ አናመልክም በሚሉትና የስደብን ነገር በሚናገሩት ላይ ከፍተኛ ቅጣት እንደሚደርስባቸው ዐዋጅ አስነገረ፡፡ ሚሳቅን፣ ሲድራቅና አብደናጎምንም በባቢሎን አውራጃ ውስጥ ሾማቸው፡፡ ከፍ ከፍም አደረጋቸው፡፡

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ልጆቿን ከእነዚህ ብላቴኖች የእምነት ፍሬ ተምረው፣ የመልአኩ ቅዱስ ገብርኤልንም ተራዳኢነት ተረድተው እግዚአብሔርን በማምለክ እንዲጸኑ ታኅሣሥ ፲፱ ቀንን ትዘክራለች፤ በታላቅ ድምቀትም ታከብረዋለች፡፡

የመላእክት አለቃ የቅዱስ ገብርኤል ምልጃና ተራዳኢነት አይለየን፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

በዓታ ለማርያም

ንጽሕተ ንጹሐን፣ ቅድስተ ቅዱሳን፣ ከተመረጡ የተመረጠች፣ ከተለዩ የተለየች፣ ከተከበሩ የተከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእናቷ ከቅድስት ሐናና ከአባቷ ቅዱስ ኢያቄም በእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ ከተወለደችበት ዕለት ግንቦት ቀን ጀምሮ በወላጆቿ ቤት ለሦስት ዓመት ከኖረች በኋላ ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ታኅሣሥ ቀን “በዓታ ለማርያም” በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡

ኢያቄምና ሐና የተሳሉትን ስእለታቸው አስታውሰው ወስደው ለቤተ እግዚአብሔር ሲሰጧትም ካህኑ ዘካርያስ ስለምግቧ ተጨነቀ፤ ሕዝቡንም ሰብስቦ ሳለ መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፤ ዘካርያስ ለእርሱ የመጣ ሀብት መስሎት ታጥቆ እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ ከስምዖን ጀምሮ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም በተራ ቢሞክሩ በተመሳሳይ መልኩ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ “ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ” ብለው ሐና እና ኢያቄም እንዲቀርቡ አደረጓቸው፤ ነገር ግን ለእነርሱም ራቀባቸው፤ ዘካርያስም ሐናን “እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ›” አላት፤ በዚያም ጊዜ ቅድስት ማርያም እናቷን ስትከተል መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መገባት፤ ከዚያም በክብር ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱና ሕዝቡም “የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር” ብለው ወደ ቤተ መቅደስ አስገቧት፡፡

ለ፲፪ ዓመታትም ቅድስት ድንግል ማርያም ሰማያዊ ኅብስትና መጠጥ እየተመገበች በቤተ መቅደስ ኖረች፡፡ በ፲፭ ዓመቷ ግን ለአቅመ ሔዋን በመድረሷ ከቤተ መቅደስ ትውጣልን በማለት አይሁድ በጠላትነት ተነሡባት፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ይህን ሰምቶ እመቤታችንን እንዲህ ብሎ ጠየቃት፤ “ኦ ወለተ እስራኤል እፎ ትፈቅዲ ትንበሪ፤ ልጄ እንደምን ሆነሽ ልትኖሪ ትወጂያለሽ?” እርሷም “ከእግዚአብሐር በታች ያለኸኝ አባት አንተ ነህ፤ በዚያውም ላይ እናት አባቴ አደራ ያሉህ አንተን ነው፤ ወደ እግዚአብሔር አመልክትልኝ” አለችው፡፡ ካህኑ ዘካርያስም በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ እንዲህ ብሎ አዘዘው፤ “ከነገደ ይሁዳ ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን በትራቸውን ሰብስበህ በቀዳማይ ሰዓተ ሌሊት ከቤተ መቅደስ አግብተህ ስትጸልይ እደር፤ በቀዳማይ ሰዓተ መዓልት አውጣው፤ ምልክትም አሳይህአለው፡፡” እርሱም እንዳለው አድርጎ በማግሥቱ በትሮቹን አውጥተው ቢያዩ የአረጋዊው ዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩ ጫፍ ላይ “ኦ ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ፥ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት” የሚል ጽሑፍ አገኙ፤ ርግብም መጥታ በራሱ ላይ ዐረፈች፤ ስለሆነም ዮሴፍ እንዲጠብቃት ተወሰነ፡፡

ከዚህም በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከቤተ መቅደስ ወጥታ እስከተሰደደችበት ወራት ድረስ ዮሴፍ ቤት ኖረች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልመኗ ክብሯ በሁላችን ላይ ይደርብን፤ አሜን፡፡

“ታገኙ ዘንድ ሩጡ” (፩ኛቆሮ. ፱፥፳፬)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በግሪክ ከነበሩ አውራጃዎች አንዷ ከሆነችው አካይያ መዲና ቆሮንቶስ ከተማ ገብቶ ለሕዝቡ ጌታ ከፅንሰቱ ጀምሮ ያደረገውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ ቢነግራቸው ብዙዎቹ ከጣዖት አምልኮ እግዚአብሔርን ወደ ማምለክ፣ ኃጢአትን ከመሥራት ጽድቅን ወደ ማድረግ ተመለሰው፤ አምነው ተጠመቁ፡፡ (ሐዋ. ፲፰፥፩–፲)

ቅዱስ ጳውሎስ የቆሮንቶስ ከተማን ሕዝብ አስተምሮ፣ አሳምኖና አጥምቆ ካቆረባቸው በኋላ ከዚያ ወጥቶ ወደ ኤፌሶን ሄደ፡፡ ነገር ግን በቆሮንቶስ ያሉ ምእመናን አስተምሮ ዋጋ ይቀበላል (ገንዘብ ይቀበላል) ብለው አሙት፡፡ ይህንን ሐሜታቸውን ሰምቶ ተስፋ ሳይቆርጥ የወንጌል አገልግሎቱን፣ ማለትም መንፈሳዊውን ትምህርት በሰፊው ቀጥሎበት ለቁመተ ሥጋ ያህል በምእመናን ገንዘብ መመገብ ምንም ቁም ነገር እንዳልሆነ፣ ምንም ሥጋዊ ጥቅም እንደማይፈልግና ገንዘብም እንዳልተቀበላቸው በትምህርቱ ውስጥ ይገልጥ ነበር፡፡ ይልቁንም ቅዱስ ጳውሎስ ይተጋ የነበረው ወንጌልን ስለማስተማር፣ ሰዎችንም ለድኅነት ለማብቃት እንደ ሕጋቸው፣ እንደ አኗኗራቸው ሁሉ እየኖረ ወንጌልን በመስበክ በዓለም በሚደረግ ሰልፍ፣ ሩጫና ሽልማት እየመሰለ ከክርስትና የሚገኘውን ክብር አስተምሯቸዋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በእሽቅድምድም ሥፍራ የሚሽቀዳደሙ ሁሉ እንደሚፋጠኑ አታውቁምን? ለቀደመው የሚደረግለት ዋጋ አለ፤ እንዲሁ እናንተም እንድታገኙ ፈጽማችሁ ሩጡ ይላል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፱፥፳፬) በጦር ሜዳ ተሰልፎ እየፎከረ፣ ጠላቱን ድል የሚያደርግ አርበኛ (ጦረኛ) ከጌታው ዘንድ ሹመት፣ ሽልማት እንዲያገኝ እንዲሁ መንፈሳዊ አርበኛ የሚሆኑ ምእመናንም በምግባር በትሩፋት እየተሸቀዳደሙ ዋጋቸውን (ክብራቸውን) ያገኙ ዘንድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አጥብቆ ይመክራቸዋል፡፡

መሮጥና ማግኘት የሚሉትን ፀንሰ ሐሳቦች ሐሳብ በሁለት መንገድ ማየት እንችላለን፡፡ አንደኛው፡- በዚህ ዓለም በሚደረግ የሩጫ ውድድር አንጻር በክርስትና የሚደረግ የሕይወት ዕድገትና መንፈሳዊ ፉክርክር ነው፡፡ አትሌቶች ሀገራቸውን ወክለው በሩጫ ተወዳድረው አሸናፊ ሆነው ተሸልመው የራሳቸውንም የሀገራቸውንም ስም በዓለም ያስጠራሉ፤ ሥጋውያን ሯጮችም ሲሮጡ በመንገዳቸው ላይ የሚደርስባቸውን ድካም የሚገጥማቸውንም መሰናክል ተቋቁመው የሚያልፉትና ለአሸናፊነት የሚበቁት በአሸናፊነታቸው የሚያገኙትን ክብርና ሽልማት ተስፋ በማድረግ ነው፡፡ ይህንንም ተስፋ ሳይጠራጠሩ እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት ይሮጣሉ፡፡

መንፈሳውያን ሯጮች የሆኑ ምእመናንም እንዲሁ በኅሊናቸው ከዚህ ዓለም ድካምና ፃዕር በኋላ ያለውን የዘለዓለም ሕይወትና የማያልፍ ተድላ ደስታን እያሰቡ ወደ መንግሥተ ሰማያት በእግረ ኃሊናቸው በጽናት ይሮጣሉ፡፡ በሕይወት መንገዳቸው ላይ ከፈቃደ ሥጋቸው፣ ከአጋንንትና ከዐላውያን ነገሥታት ሁሉ የሚደርስባቸውን የቅድስና ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ሩጫ መሰናክሎችን በፍጹም እምነትና በጽናት አሸንፈው በእግዚአብሔር ዘንድ የዘለዓለማዊው ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ተሸላሚ ይሆናሉ፡፡

ክርስቲያን ሁል ጊዜም በምግባረ ክርስትና የሚሮጥ (የሚያድግ) ነው፤ ምግባረ ክርስትና እግዚአብሔርን የምንመስልበት ሕይወት ነው፡፡ ሐዋርያው እኔ ክርስቶስን እንድመስለው እናንተም እኔን ምሰሉ እንዳለ፡፡ (፪ኛቆሮ. ፲፩፥፩) በጥንተ ፍጥረትም አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር ሰውን በአርአያችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠር” ብሎ እርሱን የመምሰል ሕይወት በሰው እንደሚገለጥ ተናግሯል፡፡ (ዘፍ. ፩፥፳፮) እግዚአብሔር ደግሞ በባሕርዩ መልካም ነው፤ ለመልካምነቱም ገደብ የለውም፡፡

ምግባረ ክርስትና ገደብ የለውም፤ ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡ እስከ አሁን የጾምኩት፣ የጸለይሁት፣ ያስቀደስኩት፣ የቈረብኩት ይበቃኛል፣ … አይባልም፡፡ ምክንያቱም የምንነሣበት እንጂ የምንደረስበት ምግባር የለምና፣ በጎነት መጨረሻ የለውም፡፡ ስለዚህ የክርስቲያን ኑሮው ሁል ጊዜ በሩጫ (በበጎ ምግባር መገሥገሥ) ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እጄን እዘረጋለሁ ያለውም ለዚህ ነው፡፡ (ፊል. ፫፥፲፫) ተክል እንደተተከለ ብቻ ከቀረ ይደርቃል እንጂ አያድግም፡፡ ስለዚህ አድጎ ፍሬ እንዲያፈራ ይኮተኮታል፤ ከአፈር፣ ከአየር እና ከውኃ ይመገባል፡፡  ከዚህም የተነሣ አድጎ፣ ለምልሞና አብቦ ያፈራል፤ ክርስቲያናዊ ሰውም እንዲሁ ነው፡፡ በሃይማኖትና በጥምቀት፣ ይተከላል፤ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይመገባል፤ በምግባር ለምልሞ፣ በትሩፋት አብቦ የክብር ፍሬ ያፈራል፡፡ ስለዚህ በክርስትና ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡

በክርስትና ሕይወት ውስጥ ምግባር ሃይማኖት እዚህ ጋር ይበቃኛል ብለን የምናቆመው ሳይሆን ዕለት ዕለት መሽቀዳደም፣ ለፍቅር፣ ለየዋሀት፣ ለቅንነት፣ ለለጋሥነት፣ ለርኅራኄ … መፎካከር ነው፡፡ ሐዋርያው ፍቅርን ተከተሏት” በማለት እንዳስተማረን፡፡ (፩ኛቆሮ. ፲፬፥፩) እንዲህ ከሆነ በሰማይ የሚገኘው ክብር ታላቅ ነው፡፡ ክብር ሁሉ በሥራ መጠን ነውና ለሁሉም እንደ ዋጋው እከፍለዋለሁ እንዳለው አምላካችን ጥቂት የሠራ ጥቂት ክብር ይቀበላል፤ አብዝቶ የሠራም አብዝቶ ይቀበላልና፡፡ (ራእ. ፳፪፥፲፪)

ሁለተኛው በጦር ሰልፍ በሚደረግ ሩጫ አንጻር በተጋድሎ የሚገኝ ጸጋን ለማመልከት ነው፡፡ ከላይ እንዳየነው የጦር ሰልፍ ሩጫ ጠላትን ድል አድርጎ ነፃነትን ማወጅ፣ ከድል በኋላ የሚገኝን ሹመትንና ሽልማትን ገንዘብ ማድረግ፣ ክብርንና አዎንታዊ የታሪክ ባለቤት መሆንን መቀዳጀት ነው፡፡ ስለዚህ ሥጋውያን ጦረኞች እግራቸውን ለጠጠር፣ ግንባራቸውን ለጦር ሰጥተው ከድል በኋላ ስለሚያገኙት ሽልማት እኔ ልዝመት እኔ ልዝመት ብለው ይሽቀዳደማሉ፡፡

ከተጋድሎ በኋላ የሚያገኘውን ክብር የሚያስብ ክርስቲያንም እንደዚሁ ዲያብሎስ ያሰለፈውን ጦር ድል ለመንሣት ይሰለፋል፣ ሞትንም አይፈራም፡፡ ብእሲ ዘይሬኢ አክሊላቲሁ ኢይሜምእ፤ አክሊሉን የሚያይ ሰው ወደ ኋላ አያፈገፍግም በማለት እንዳስተማረን፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ተግሣጽ) ከፊቱ የሚጠብቀውን ክብርና ሽልማት የሚያስብ ተጋዳይ በአሁናዊ መከራው አይማረርም፡፡ መዝሙረኛው ዳዊት እንዲህ ይላል እለ ይዘርዑ በአንብዕ ወበሐሴት የዐርሩ፤ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ ወጾሩ ዘርዖሙ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ ወጾሩ ከላስስቲሆሙ፤ በልቅሶ(በዕንባ) የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ፤ በሄዱጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዷቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ እንዲል፡፡ (መዝ. ፻፳፭፥፮-፰)

በክረምት የሚዘራ ገበሬ ጠዋት ሲወጣ በላይ ዝናቡ ይወርድበታል፤ በታች ቅዝቃዜው፣ ጭቃውና ጎርፉ ይፈራረቁበታል፤ ስለዚህ በመከራ ይዘራል፡፡ የዘራው አፍርቶ አጭዶ ሲከምረው ግን መከራውን ረስቶ ጨምሬ ዘርቼ ቢሆን ኖሮ ይላል፤ እሸቱን እየበላ ነዶውን ሲሰበስብም ደስ ይለዋል፡፡ እንዲሁ በክርስትና ሕይወታቸው የጸኑ ሰማዕታት ከተሳለ ስለት፣ ከነደደ እሳት ሲገቡ መከራው ይሰማቸዋል፤ ጻድቃን ፍትወታት እኵያት ኃጣውእ ርኵሳት ሕሊናቸውን ያስጨንቃቸዋል፣ ድል ከነሡ በኋላ ግን ሰማያዊ አክሊልን ተቀዳጅተው በተድላ በደስታ ይኖራሉ፡፡

ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ በአካለ ነፍስ ሆኖ መነኮሳት በአክናፈ እሳት ወደ ኢየሩሳሌም ሲገቡ አይቶ አንድን አባት «ሰላም ለክሙ ብፁዓን መነኮሳት፤ ንዑዳን ክቡራን መነኮሳት ሆይ ሰላም ለእናንተ ይሁን»  አለው፡፡ መነኮሱም አንተም እንጂ ንዑድ ክቡር ነህ በዘመንህ ቀርነ ሃይማኖት ቆሞልሀልና አለው፡፡ ቆስጠንጢኖስም ይህንን አውቄስ ቢሆን መንግሥቴን ትቼ እንደ እናንተ በምናኔ በኖርሁ ነበር ብሎታል፡፡ (ፊልክስዩስ) ስለዚህ የዚህን ዓለም መከራና ሥቃይ የወዲያኛውን ክብር ያስረሳዋል፡፡ በዚህ ዓለም ሴት ልጅ በጭንቅና በምጥ ስትወልድ ታዝናለች ከወለደች በኋላ ግን ደስ ይላታል፤ ከወደለች በኋላ ግን ጭንቋንና ምጧን አታስበውም፤ ምክንያቱም ጨንቋንና ምጧን በልጇ ስለምትረሳው፡፡ (ዮሐ. ፲፮፥፳፩) ስለዚህ ክርስቲያኖችም የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ በተጋድሎና በትዕግሥት ሊያልፉት ይገባል፡፡ እንዲህም ከሆነ በሰው ኅሊና የማይተረጎም ሰማያዊ ክብርን ያገኛሉ፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወት አክሊልንም እሰጥሀለሁ እንዲል፡፡ (ራእ. ፫፥፲) ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት በተጋድሏቸውና በአሸናፊነታቸው ከሚቀበሉት ክብር አንጻር አሁን የሚያገኛቸው መከራ ኢምንት ነው፡፡ ስለዚህ ሰማያዊውን ክብር ለማግኘት መንፈሳዊውን ሩጫ መሮጥ ከኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር፡፡

ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል ሁለት

በዲ/ መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

የጾም ዓይነቶች

የጾም ዓይነቶች ሁለት ናቸው እነርሱም የአዋጅ እና የፈቃድ በመባል ይታወቃሉ፡፡

. የዐዋጅ ጾም

የዐዋጅ ጾም የሚባሉት በዐዋጅ ለሁሉም ሰው ማለት ከሰባት ዓመት በላይ ለሆነ ሰው ሁሉ የሚታወጅ እና በይፋ ሁሉም ተባብሮ ስለሚጾማቸው ነው፡፡ “በጽዮን መለከትን ንፉ፥ ጾምንም ቀድሱ፥ ጉባኤውንም አውጁ፥” (ኢዩ ፪፥፲፭) እንደተባለ አንዴ በቤተ ክርስቲያን ታውጆ ሥርዓት ተሠርቶለት የሚጾም ስለ ሆነ የአዋጅ ጾም ይባላል፡፡ የአዋጅ ጾም በማለት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምታውጃቸው እና ሁላችን በጋራ የምንጾማቸው አጽዋማት ሰባት ሲሆኑ እንደሚከተለው እንመለከታቸዋለን፡-

  1. ዓቢይ ጾም (ጾመ ሁዳድ)
  2. ጾመ ድኅነት (ዓርብ እና ረቡዕ)
  3. ጾመ ሐዋርያት (የሰኔ ጾም)
  4. ጾመ ፍልሰታ
  5. ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)
  6. ጾመ ነነዌ
  7. ጾመ ጋድ ናቸው፡፡

. የፈቃድ ጾም

የፈቃድ ጾም የሚባለው ሁሉም ሰው በዐዋጅ ሳይታዘዝ በፈቃዳችን የምንጾማቸው ናቸው፡፡ በቀኖና የሚሰጠን ጾም የሚመደበው ከዚህ ውስጥ ነው፡፡ አንዳዴም በተለየ ሁኔታ ለራሳችን የምንጾመው ጾምም የፈቃድ ይባላል፡፡ ለምሳሌ ጾመ ዮዲት (ጳጉሜን ላይ የሚጾም) እና ጾመ ጽጌ የሚጾሙ አሉ፤ እኒህም የፈቃድ አጽዋማት ናቸው፡፡

ውድ ተማሪዎች ጾም ፍቅርን ለእግዚአብሔር መግለጫ በመሆኑ ከልባችን ወደነው መጾም ይገባል፡፡ በጾም ስሜትን ራስን እንገዛበታለን፡፡ ጾም መንፈሳዊ ኃይልን ታጎናጽፋለች፤ አጋንንትን ለማራቅ እጅግ ትጠቅመናለች እንዲሁም ለመንፈሳዊ አገልግሎት የበረታን ታደርገናለች እና በአግባቡ በመጾም የምታሰጠውን ዋጋ ለማግኘት እንትጋ፡፡

እንደ ግብዞች አትጠውልጉ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዴት መጾም እንዳለብን የተራራውን ትምህርት ባስተማረበት ወቅት እንዲህ በማለት ተናገሮ እንመለከታለን “ስትጦሙም፥ እንደግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮)። በዚህ ንባብ ግብዞች የሚለውን ቃል በሁለት መልኩ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስቀምጦት ይገኛል። እነዚህም፡-

 ፩. መጦመቸው እንዲታወቅላቸው ፊታቸውን የሚያጠፉ እንዲሁም ይጠወልጋሉ። እነዚህ ጦማቸውን ዋጋ ለሚከፍል እግዚአብሔር ከማሳየት ይልቅ ለሰዎች አድናቆት ለማግኘት ሲሉ ብቻ የጾምን ዓላማ ያጠፉታል።

፪. ሳይጾሙ እንደጾሙ የሚያስመስሉ ከንፈራቸውን የሚያደርቁ ግብዝ ተብለው ተጠርተዋል። የምንጾመው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትን ለማድረግ ነው እንጂ ውዳሴ ከንቱን ለማግኘት አይደለም፤ በሁለቱም መልክ የተገለጡት ግብዞች ግን የጾምን ዓላማ የረሱና ያልተገነዘቡ ናቸው። በግብዝነት የሚገኘው ደስታ ጊዜያዊና ወዲያው የሚረሳ ነው ሆኖም ቅጣቱ ከባድ መሆኑን ዐውቆ መጠንቀቅ ይገባል።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በተለይ በልቶ ማስመሰል ውዳሴ ከንቱን መፈለግ ብቻ ሳይሆን ውሸትንም በውስጡ የያዘ ነውና ከግብዝነት በመራቅ በእውነት ለጾም ሕግና ሥርዓት ልንገዛ ይገባል። ለቤተሰብ ለጓደኛ ለቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ራሳችንን በውሸት ሕጋዊ አድርገን ለማሳየት ስንል መንግሥተ እግዚአብሔርን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይገባል። ለሰው ጾመኛ ከመምሰል በመታቀብ ዋጋ ለሚከፍለው ጌታ ራስን ማሳየት ያስፈልጋል። ፊትን በማጥቆር ከመጾም ፊትን ከእግዚአብሔር የሚያገኙትን ዋጋ በእምነት በተስፋ በመጠበቅ ብሩህ ማድረግ በእጅጉ ይገባል። ጌታችን ጾሞ እንዴት መጾም እንዳለብን አስገንዝቦናል በዚያው መሠረት በመጾም ሥርዓትን ልንፈጽም ይገባል።

ክርስቶስ አምላካችን ዐርባ ቀንና ሌሊት በመጾም ጾም የመልካም ሥራ መጀመሪያ እንድትሆን ሰጥቶናል። እኛም የሐዋርያቱን ትውፊትና ኑሮ መሠረት በማድረግ ያማረ የጾም ሕግን ከትውልድ ትውልድ እንቀባበለዋለን። ጌታችን የጾመው በቁዔት አገኝበታለሁ ብሎ ሳይሆን አጋንንትን፣ የኃጢአት ሥሮች የተባሉ ትዕቢት፣ ስስት እና ፍቅረ ነዋይን የምናሸንፍበትን ሕግ ሊሠራልን እና ተግባሩን ሊያመለክተን ነው እንጂ ጾማችሁን ሁሉ ጾሜላችኋለሁ ከዚህ በኋላ መጾም አይጠበቅባችሁም ለማለት አይደለም።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በግቢ ሕይወታችሁ ከብዙ ማኅበረሰብ ጋር እንደመኖራችሁ በሃይማኖት ከማይመስሉን በተለይ ከመናፍቃን ጥያቄ ሊቀርብልን ይችላል። ለምሳሌ አጽዋማት ለድኅነት አያስፈልጉም አንዴ ክርስቶስ ጾሞልናል፤ በዚህ ጊዜ እንድትጾሙ የተጻፈው የት ነው? ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም የሚለውን ሕግ ጥሳችኋል ሊሉን ይችላሉ።

ውድ ተማሪዎች ከመናፍቃን ጋር ያለን ልዩነት ሰፊና የመዳናችን መንገድ ላይ መሆኑን ልብ ማለት አለባችሁ ይህ ማለት ከላይ የጠቀስነው ንግግራቸው የሚመነጨው እምነት ብቻ ከሚለው አስተምሮአቸው ነው። ምግባር ለድኅነት አያስፈልግም በጸጋው ብቻ ድነናል ከሚለው አቋማቸው መሆኑን በመረዳት ከእነርሱ መራቅ ሐሳባቸውን አለመስማት ይኖርብናል። ምክንያቱም ጾም ትእዛዘ እግዚአብሔር ናት፤ ምግባር የእምነት ነፍስ ናትና “መጽሐፍም፦ አብርሃምም እግዚአብሔርን አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቈጠረለት ያለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ። ሰው በእምነት ብቻ ሳይሆን በሥራ እንዲጸድቅ ታያላችሁ። … ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደ ሆነ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው።” (ያዕ. ፪፥፳፫-፳፮) እንደተባለ። እምነት ከምግባር ተዋሕዶ ሊገኝ ግድ ነው። እንግዲህ ከምግባራት ቀዳሚዋ ጾም መሆንዋ ደግሞ ሊዘነጋ አይገባውም። ጌታችን ስለ ሆድ ማሰብ ሞት እንደሆነ አስተምሮናል አስቀድመን ማሰብ የሚገባን ስለ ጽድቅ መሆኑንም አሳስቦናል “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፥ ይጠግባሉና።” (ማቴ. ፭፥፮)። “ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?” (ማቴ. ፮፥፳፭)።

ስለዚህ ክርስቶስ ጾሞልሃል የሚለውን የሰይጣን ትምህርት ትተን “ከመዝ ግበሩ፤ እንዲህ አድቡ” የሚለውን የክርስቶስን ድምጽ በመስማት የተወልንን የአርአያነት መንገድ በመከተል እውነተኛ በጎቹ ልንሆን ይገባል። “ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል።” (ማቴ. ፮፥፴፫) “ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮።)  ‘ይህም ሁሉ’ የተባለው ምግብን እና መሰሎቹን ነው። ክርስቶስ አትጹሙ አላለም ስትጾሙ እንደ ግብዞች አትሁኑ በማለት አጿጿሙን ተናገረ እንጂ ስለዚህ ጾም ክርስቶሳዊ ትእዛዝ ነው።

ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም በማለት ሆድን አምላክ በማድረግ ሊሾሙብን እንደ ሔዋን ራቁታችን ሆነን ገነትን መንግሥተ ሰማይን አጥተን እንዳንጠፋ መጠንቀቅ አለብን።  ውድ ተማሪዎች ተመልከቱ ጌታችን ስለ እጅ ንጽሕና ሲጨነቁ ስለ አመጋገብ ወጋቸው ከሕገ መጽሐፍ በላይ ሲያሳስባቸው ተመልክቶ የተናገራቸውን ነገር “እርሱም፦ እናንተ ደግሞ እንደዚህ የማታስተውሉ ናችሁን? ከውጭ ወደ ሰው የሚገባ ሊያረክሰው ምንም እንዳይችል አትመለከቱምን? ወደ ሆድ ገብቶ ወደ እዳሪ ይወጣል እንጂ ወደ ልብ አይገባምና አላቸው። እርሱም አለ፦ ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው። ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ ሐሳብ፥ ዝሙት፥ መስረቅ፥ መግደል፥ ምንዝርነት፥ መጐምጀት፥ ክፋት፥ ተንኰል፥ መዳራት፥ ምቀኝነት፥ ስድብ፥ ትዕቢት፥ ስንፍና ናቸውና፤ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል ሰውን ያረክሰዋል።” (ማር. ፯፥፲፰-፳፫)። ተማሪዎች ተመለከታችሁን? ይህ ጾምን የሚያጸና እንጂ የሚሽር ነውን? አይደለም ምክንያቱም ጾም ማለት ከምግብና ከሚያረክሶ ነገሮች ሁሉ መራቅ ነው።

በአጠቃላይ ከመናፍቃን ራሳችንን እንጠብቅ በተዋበች የጾም ሕግ ጽድቅን እንፈልግ፤ ከተድላ ደስታ በመራቅ ከእግዚአብሔር ጋር አንድ እንሁን “ትእዛዙንም የሚጠብቅ በእርሱ ይኖራል እርሱም ይኖርበታል፤ በዚህም በእኛ እንዲኖር ከሰጠን ከመንፈሱ እናውቃለን።” (፩ኛዮሐ. ፫፥፳፬ እንደተባለ። በተጨማሪም ምሳሌውን አርአያነቱን በማስተዋል እንከተል “በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል።” (፩ኛዮሐ. ፪፥፮) ተብሎ እንደተጠቀሰ።

የአጽዋማትን ጊዜ የተመለከተውን ልንወዛገብበት አይገባም። ውድ ተማሪዎች የእኛ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሥርዓተ አምልኮ ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ አይደለም ይልቁንም የቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት፣ ትውፊትና ከሐዋርያት ጀምሮ ያሉ አበው ትምህርት ሕይወት እንደ ምንጭ የሚወሰድ በመሆኑ ከበቂ በላይ ማስረጃ አለን። በሐዲስ ኪዳን ቀኖና ውስጥ ያሉ ስምንቱ መጻሕፍት ሁሉም ላይ የጾም ጊዜ ሥርዓት በቀኖናው ተጽፎ እንደሚገኝ መዘንጋት አይገባም።  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Top of Form

Bottom of Form

Top of Form

Bottom of Form

ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል አንድ

በዲ/ መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

ጾም ለሰውነት የሚያምረውን እና የሚያስጎመዠውን ነገር ሁሉ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ብሎ  መተው፣ ራስን በመግዛት ጣዕመ ዓለምን በመናቅ እግዚአብሔርን መከተል ማለት ነው፡፡ ጾም  ራስን ከክፉ ሥራዎች ሁሉ በማሸሽ የመንፈሳዊ ተጋድሎ መፈጸሚያ መሣሪያ እና የሥጋ ልጓም ነው፡፡ መንፈሳዊ በረከትን ለማግኘት ለትእዛዘ እግዚአብሔር ራስን ማስገዛት ነው፡፡ ፍጹም የሆነ የእግዚአብሔርን ርዳታ ማግኛ የፍቅር መንገድ ነው፡፡ ጾም ሃይማኖትን መግለጫ በተግባር ማሳያ መታመኛ መሣሪያ ነው፡፡ ጾም፤ ወዶ ፈቅዶ ምግብን በጊዜ ገደብ ጥሉላትን በቀናት/በወራት ገደብ እንዲሁም ነፍስን ከሚያሳድፉ ክፉ ሥራዎች መከልከል ነው፡፡ ለእግዚአብሔር ያለን ፍጹም ፍቅር የሚገለጠው በጾም በጸሎት እና ምጽዋት ነው፡፡ የቀና እና የተስተካከለ መንፈሳዊ ሕይወትን ከሚያደናቅፉ ማናቸውም እኩይ ተግባራት መራቅ እና መከልከል ጾም ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ነፍስን ሊያቆስላት የሚችለው ምንድን ነው? ስንል መልሱ የሥጋ ፈቃድን መፈጸም፣ በደል፣ ኃጢአትነው የሚል ይሆናል፡፡ ሰው ተማሪ ቢሆን ሠራተኛም ቢሆን በምንም ዓይነት ሥራ እና ሁኔታ ላይ ቢሆን ክርስቲያናዊ ሕይወቱን ለማረም ዕለት ዕለት መንፈሳዊ ተግባራትን መተግበር ያስፈልጋል፡፡ በይበልጥ ሐዋርያት የሥራ መጀመሪያ ያደረጓትን ጾምን እኛም አጥብቀን ልንይዝ ይገባል፡፡ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፥ ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው።” (ሮሜ. ፰፥፮)፡፡ ሥራችንን ክርስቲያናዊ ጉዞአችንን ፍጹም የሚያደርግልን ጾም ነው፡፡ ለዚህም ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን እንደ ምሳሌ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ስለዚህ ተማሪዎች ቀዳሚት ትእዛዝ የሆነች ሕግን ገንዘብ በማድረግ ሕይወታችንን ሰማያዊ ዋጋ በሚያሰጥ መልክ እንምራ፡፡

ጾምን ለምን እንጾማለን?

ጾም በመጀመሪያ ለሰው የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ የሰው ልጅ ቢመራበት የዘላለምን ሕይወት የሚወርስበት ልዩ የእግዚአብሔር የፍቅር ሕግ ነው፡፡ ሰው ፍትወቱን በዚህች ባማረች ሕግ ገዝቶ ዓይኑን ክፉ ከማየት፣ ጆሮውን ክፉ ከመስማት፣ ምላሱን ክፉ ከመናገር ከማማት፣ እግሩን እጁን ከመስረቅ ደም ለማፍሰስ ወደ ክፉ ከመገስገስ ቢከለክል ዋጋው ምንኛ ያማር ይሆን ነበር፡፡ እኛ በዚህ ዘመን ያለን ወጣቶች በዓለሙ ካለ ክፋት የትኛውን ተጸይፈን እንተዋለን? ዘመነኛው ቴክኖሎጂ ያመጣልንን ማኅበራዊ ሚዲያ በመጠቀም ክፉኛ ወደሚያቆስለን ለገሃነም ወደሚሰጠን የሥጋ ሥራ አዘንብለናል፡፡ ነገር ግን የተሰጠንን በጎ አእምሮ በመጠቀም ወደ ኃጢአት ከመሄድ ራሳችንን ልንጠብቅ እና ልናነጻ ይገባል፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ የጾምን ጥቅም በቅደም ተከተል እንመልከት፡–  

. ኃይለ እግዚአብሔርን ለማግኘት

አብዝቶ መመገብ ፈቃደ ሥጋ በፈቃደ ነፍሳችን ላይ እንዲሰለጥን ሰፊ በር ይከፍታል፡፡ ፍትወታተ ሥጋ እንዲሰለጥኑብንም ዋነኛ ሞተራቸው በመሆን ይጠቀሳል፡፡ ጥጋብን፣ ትዕቢትን፣ ንዝህላልነትን፣ ዝሙትን በማምጣት መንፈሳዊ ፍሬን እንዳናፈራ ያግደናል፡፡ ሰዶምን በእሳት እንድትቃጠል ካደረጓት ምክንያቶች አንዱ እንጀራን መጥገብ እንደሆነ (ሕዝ. ፲፮፥፵፱) ተገልጧል፡፡ ፈቃደ ሥጋችን በፈቃደ ነፍሳችን ላይ ኃይል እንዳይኖረው ጾም መጾም እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነቢዩ ዳንኤል ከሦስቱ ሕፃናት ጋር ከኢየሩሳሌም ተማርከው ወደ ናቡከደነፆር ግዛት ከተወሰዱ ዕብራውያን ወጣቶች መካከል ተመርጦ ሦስት ዓመት በከለዳውያን ትምህርት ቤት የከለዳውያንን ጥንቆላ (ኮከበ ቆጣሪ) ሕልም መፍታት፣ ቋንቋ እና ባህላቸውን ከሦስቱ ወጣቶች ጋር በመሆን እንዲያጠኑ በተቃራኒው ደግሞ የራሳቸው የሆነውን የእስራኤልን እምነት እና ባሕል እንዲረሱ በተደረጉበት ጊዜ ዳንኤል እንዲመገቡ የተፈቀዱላቸውን የንጉሡን ምግብ እና መጠጥ ከመብላት እንቢ አለ፤ የአሕዛብ ምግብ እንደሚያረክሰው አስቧልና፡፡ ይልቁንም ቆሎ እየበሉ ይማሩ እንደነበር ትንቢተ ዳንኤል ያስገነዝበናል፡፡

ሰውነታቸው ቅቤን በማጣት ቢነጣም ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸው ኅብረት በጣም ከፍተኛ ነበር፡፡ በጾም መጠንከራቸው በትምህርታቸው ጎበዝ እና በንጉሥ ፊት ሞገስ ያላቸው የሚመረጡ ከመሆን አላገዳቸውም፤ እንዲያውም ከሌሎቹ በላይ ሞገስ እንዲኖራቸው በሀገሪቱ ውስጥ ሥልጣን እንዲያገኙ፣ የተደበቀን ምሥጢር በመግለጥ የበረቱ እንዲሆኑ አደረጋቸው እንጂ፡፡ እግዚአብሔርም በነገር ሁሉ ይረዳቸውና ከጎናቸው ይሆንላቸው እንደነበረ መጽሐፍ ያስገነዝበናል፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው በጾም በመጽናታቸው እና ከኃጢአት ራሳቸውን በመጠበቃቸው ባገኙት ኃይለ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ስለዚህ ወጣቶች (የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች) ስንጾም በትምህርታችን ልንደክም እንደምንችል እያሰብን እግዚአብሔር ከሚሰጠን ኃይል እና ጥበብ እንዳንርቅ ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡

ክርስቲያን መንፈሳዊ ተግባራትን በተመቸው ቀን ብቻ የሚተገብር አይደለም በጊዜውም ያለጊዜውም ጸንቶ የሚገኝ ነው እንጂ፡፡ ጾም ሌሎችን ምግባራት (ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት…) ለመፈጸም ፍጹም ኃይልን የምትሠጥ በጎ ተግባር ናት፡፡ የመንፈሳውያን ኃይል የሆኑትን ትዕግሥትን፣ ቸርነትን፣ በጎነትን፣ ራስን መግዛትንወዘተ ገንዘብ ለማድረግ ጾም ዋና መሣሪያችን ነው እና ገንዘብ እናድርገው፡፡

. ተጋድሎን መፈጸሚያ ነው

በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምንጋደለው ከመንፈሳውያን የክፋት ሠራዊት ጋር እንደሆነ እንዲህ በማለት ተነግሮናልመጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።” (ኤፌ. ፮፥፲፪)፡፡ ለመጋደል የተዘጋጀ ሰው ደግሞ መሣሪያ እንደሚያስፈልገው  ይታወቃል ስለዚህ ጾም ከሁሉ ቀድሞ የሚገኝ ተጋድሎ የመፈጸሚያ መሣሪያ ነው፡፡ በቀንና በሌሊት ከቤተ መቅደስ ሳይለዩ እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ያገለገሉ ቅዱሳን የክፋት ሠራዊትን ድል የማድረግ ኃይልን ተጎናጽፈዋል፡፡ ልባችን በጸጋ እንጂ በምግብ እንዳይጸና ሐዋርያው አስጠንቅቆናል፤ ምግብን አብዝቶ በመብላት እና ለምግብ በማድላት የተጎዳ እንጂ የተጠቀመ እንደሌለ አስተምሮናልና (ዕብ. ፲፫፥፱)፡፡

የተወደዳችሁ ተማሪዎች ተድላና ደስታን በመፈለግ መንግሥተ እግዚአብሔር አትወረስም፡፡ እስኪ ሊቀ ነቢያት ሙሴን እንመልከት ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከክርስቶስ ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መራብን መረጠ፡፡ በዚህ ምክንያት ከሞቀ መኖሪያ ከቤተ መንግሥት ለስደት ተዳረገ፤ ተራበም፤ ተጠማም የሚያገኘውን ዋጋ በዚያ ዘመን ሆኖ ተመልክቷልና (ዕብ. ፲፩፥፳፬፳፭)፡፡ ይህን በማድረጉ ተጎዳ ወይስ ተጠቀመ? በጣም ተጠቀመ እንጂ የተጎዳው አንዳች አልነበረም፡፡ ሙሴ ለዐርባ ቀናት ከምግብ በመከልከል ከእግዚአብሔር ጋር በመነጋገር ሕግጋትን ታቦትን ከአምላከ ቅዱሳን መቀበል የቻለው በጾም በመጋደሉ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ሰማይን እስከ መለጎም የደረሰ ሥልጣንን ማግኘት የቻለው ዐርባ ቀን እና ሌሊት ለመጾም ይከብድብኛል ሰውነቴ ይከሳል ሳይል ሳይፈራ በጾም በጸሎት በመቆሙ ከክፉዎች ጋር ባለመተባበሩ ነው፡፡ ስለዚህ በረጅሙ የክርስትና ጉዙአችን ውስጥ ጾም በጣም ወሳኝ ነገር መሆኑን ማሰብ እንደሚገባ ልንጋደል ይገባል፡፡ የሥጋችን ፈቃድ ለመግዛት በምናደርገው ተጋድሎ ውስጥ ጾም ጉልህ ሚና አለው፡፡ ጾም የነፍስን ቁስል ትፈውሳለች፤ የሥጋንም ፈቃድ ወይም ፍላጎት ዝም ጸጥ ታሰኛለች እና ለተጋድሎ ጠቃሚ መሣሪያ ናት፡፡

. እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመኖር

የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰው ሕያው ሆኖ እንዲኖር ነው፡፡ ማንም በሞት እንዲጠፋ ከገነት ከመንግሥተ ሰማይ እንዲጎድል አይፈልግም፡፡ የሰው ትልቁ ተስፋ መንግሥተ እግዚአብሔርን ወርሶ ዘለዓለማዊ መሆን ነው፡፡ የሕይወት መውጫው ልባችን እንደሆነ መጽሐፍ ይነግረናልአጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና።” (ምሳ. ፬፥፳፫) አዳም አባታችን አትብላ የምትለውን ሕግ በመሻሩ የሥጋ ፈቃዱን በመፈጸም ከፈቃደ እግዚአብሔር ርቆ በእግረ ሞት ተረግጧል፤ እኛም ከዚህ ሕግ ፈቀቅ ብንል የአዳም ዕጣ ሊገጥመን እንደሚችል ጥርጥር የለውም፡፡ ታዲያ ፈቃደ እግዚአብሔር እየፈጸምን ለመኖር ምን ያስፈልገናል? ካልን ራስን መግዛት የምታስችለውን ጾምን ገንዘብ ማድረግ ነው፡፡ (ኢዩ. ፪፥፲፪) በፍጹም ልብ በመጾም ወደ እርሱ እንድንመለስ መማጸኑ እግዚአብሔር የሚወዳት ጾም ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም የሚያስችል ትልቅ ኃይል እንዳላት ያመለክታል፡፡ ጾም በሰው ጥበብ የተጀመረች ሕግ አይደለችም ምን እንደምትጠቅም የሚያውቅ አምላክ ፈቃዱን እንድንፈጽምባት የሠራት ሕግ ናት እንጂ፡፡

በመጀመሪያ ከመጾማችን በፊት ጾም አድካሚ እና ጎጂ ሕግ ነው ብለን ከመሳት ራሳችንን ልንጠብቅ ይገባል፡፡ ይህ ሕግ የፍቅር ሕግ ነው፤ ከአምላካችን ጋር ኅብረት የምናደርግበት የምሕረት ዓይኑ እንድትመለከተን የምታደርግ ሕግ ስለሆነች በጾም ወደ ፈጣሪ መመለስን እንደ መጎዳት ማሰብ ፈጽሞ ስህተትን ያስከትላልና እንጠንቀቅ፡፡ ፈተና እየተፈተንም ቢሆን እያጠናን ልወድቅ እችላለሁ በሚል ፍርሃት አምላክን ከማሳዘን ከመንግሥቱ ከመጉደል መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡

በአጠቃላይ የክርስትና ዋና ዓላማ በእንግድነት በዚህ ዓለም ባለንበት ዘመን ከፈቃደ ሥጋ መራቅ፤ ነፍስና ሥጋን ማንጻትና የእግዚአብሔር ማደሪያ ማድረግ ነው። ይህ ደግሞ በብዙ ድካምና ተጋድሎ የሚሳካ ነው። በመጽሐፍ “. . . ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል።” (ሐዋ. ፲፬፥፳፪) እንደተባለ መንገዱ የተደላደለ ሳይሆን ብዙ ተጋድሎ የሚያስፈልገው መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል። ገዢዋ የሥጋ ፈቃድ የሆነባት ሰውነት ሞት ያገኛታልበገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፥ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘለዓለምን ሕይወት ያጭዳል።” (ገላ. ፮፥፰) እንዲል ሥጋን በጾም ለነፍስ ማስገዛት ሕይወትን ያስገኛል።

እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፤ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ። በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና። ” (ሮሜ. ፰፥ ፲፫፲፬) ጾም ፈጽሞ የሥጋ ሥራን ማስወገጃ፣ ተጋድሎን መፈጸሚያ መንገድ ነው።  “መብል ለሆድ ነው፥ ሆድም ለመብል ነው፤ እግዚአብሔር ግን ይህንም ያንም ያጠፋቸዋል። ሥጋ ግን ለጌታ ነው እንጂ ለዝሙት አይደለም፤ ጌታም ለሥጋ ነው” (፩ኛቆሮ. ፮፥፲፫) ሥጋዊ መብልን በመብላት የሚሠራ ጽድቅ የለም፤ ይልቁንም ብዙ ምግብ ለዝሙት፣ ለትዕቢት የሚያጋልጥ በመሆኑ በጾም ሰውነታችንን ከትዕቢት እንዲሁም ከዝሙት እንጠብቅ። ይህንን ካደረግን ከሆድ ጋር ከመጥፋት ራሳችንን እንታደጋለን። መንፈሳዊ ፍሬን ለማፍራት የምትቀድም ምግባር ጾም ናት ስለዚህ አጥብቀን እንፈልጋት እንያዛትም።የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችምና።” (ሮሜ. ፲፬፥፲፯) በጾም የምናገኛት ተስፋችን ምን እንደምትመስል በታወቀ ጊዜ ከምግብና ከክፋት በመራቅ የምንገባባት መሆኗንስ ተረዳን? ሰው ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ የሚያስፈልገው ጾም እንጂ ምግብ አይደለምመብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም፤ ባንበላም ምንም አይጎድለንም ብንበላም ምንም አይተርፈንም።” (፩ኛቆሮ. ፰፥፰) እንደተባለ። የምግብ ኃይል ለሥጋ ነው የጾም ኃይሏ ግን ለነፍስ ነውየክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑት ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ።” (ገላ. ፭፥፳) የተባለውን እናስተውል።

ይቆየን

 

ጾመ ነቢያት

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሰባት የዐዋጅ አጽዋማትን በቀናት፣ በሳምንታትና በወራት ቀምራ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ እንጠቀምበት ዘንድ ደንግጋ አበርክታለች፡፡ ከእነዚህ አጽዋማት መካከል ደግሞ ጾመ ነቢያት አንዱ ሲሆን ኦርቶዶክሳውያን ከኅዳር ፲፭ እስከ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ዋዜማ ድረስ የምንጾመው ጾም ነው፡፡  

እግዚአብሔር ለአዳም አባታችን በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ይህንን ዓለም ያድን ዘንድ የሰውን ሥጋ ለብሶ እንደሚወለድ ነቢያት በትንቢት መነጽርነት ተመልክተው ተናግረዋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፣ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፤ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” (ኢሳ. ፯፥፥፲፬) እንዲል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩከአጥቢያ ኮከብ አስቀድሞ ከሆድ ወለድሁህተብሎ እንደተጻፈው፡፡ (መዝ. ፻፱፥፫) በተጨማሪምእነሆ በኤፍራታ ሰማነው፤ ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው፤ እንግዲህስ ወደ እግዚአብሔር ማደሪያዎች እንገባለን፤ የጌታችን እግሮቹ በሚቆሙበት ቦታ እንሰግዳለን” (መዝ. ፻፴፩፥፮) በማለትይወርዳል፣ ይወለዳልየሚለውን የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይህን ዓለም ለማዳን በሥጋ መምጣት ተናግረዋል፡፡ ነቢያት በዚህ ብቻ ሳያበቁ ስለ ስደቱ፣ ስለ ጥምቀቱ፣ ወንጌልን ስለመስበኩ፣ መከራ ስለ መቀበሉ፣ ስለ ሞቱ፣ ስለ ትንሣኤው፣ ዕርገቱና ዳግም ምጽዓቱ በትንቢት ተናግረዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነቢያት የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መወለድ እየናፈቁ ጾመውታልና ጾመ ነቢያት ተብሏል፡፡

የነቢያት ትንቢት ፍጻሜውን አግኝቶ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜም የአዳም ተስፋው ተፈጽሟልናጾመ አዳምእየተባለም ይጠራል፡፡ የጾሙ መጨረሻም በዓለ ልደት በመሆኑጾመ ልደትይባላል፡፡ የነቢያት ትንቢት ተፈጽሞ ጨለማውን ዓለም በወንጌል ብርሃንነት (በስብከት) አጣፍጧልናጾመ ስብከትተብሎ ይጠራል፡፡

እንደዚሁም ሐዋርያት በዓለ ልደቱን እንዴት ዝም ብለን እናከብረዋለን? ነቢያት አባቶቻችንይወርዳል ይወለዳልብለው በተስፋ እየናፈቁ ጾመውታል፤ በዓለ ትንሣኤውን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብረዋለን፤ በዓለ ልደቱንም ጾመን በረከት እናገኝበታለን ሲሉ ጾመውታልናጾመ ሐዋርያትይባላል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን እንደምትፀንስ ካበሠራት በኋላ “ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?” በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ ጾማዋለችና ይህ ጾምጾመ ማርያምእየተባለም ይጠራል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በነቢያት ጾም ነቢያት፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ሐዋርያት፣ ጻድቃን ሰማዕታት ጾመው በረከት አግኝተውበታልና እኛ ምእመናንም በረከትን እናገኝ ዘንድ መጾም እንደሚገባን የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ ጾመን፣ ጸልየን የበረከቱ ተሳታፊዎች ያድርገን፡፡ አሜን፡፡  

ምንጭ፡

ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡

ጾምና ምጽዋት፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯፶፡፡