ቀዳም_ሥዑር

ከመምህር አዲሱ በዛብህ
የማይሞተው አምላካችን በፈቃዱ ቅድስት ነፍሱን ከሥጋው ከለየ በኋላ ሰማይና ምድር የማይችሉት አምላካችን እኛን ያስነሣ እና ነጻነትን ይሰጠን ዘንድ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ነጻ ሲያወጣ በአካለ ሥጋ ከመለኮቱ ያለመለያየት በመቃብር ሦስት ቀን ሦስት ሌሊት ሙስና መቃብር ሳያገኘው ቆይቷል።
ይህንን ሊቁ ቅዱስ ቄርሎስ ሲያስረዳ እንዲህ ይላል”ነፍሱን በሲኦል አልተወም ሥጋውም ሙስና መቃብርን አላየም መለኮቱ ከሁለቱም አልተለየም ሁለንተናው ከነፍስ ጋር በሲኦል ነበር። በሲኦል ለጻድቃን የምሥራችን አበሠረ፤ ሁለንተናው ከሥጋ ጋር በመቃብር ነበር እንጂ በቦታው ሁሉ ምሉእ ነውና” (ሃይ. አበ ዘቄርሎስ ፸፩፥፲፭-፲፮)
ለሁላችን የማያልፍ ድኅነትን ፣ ሥርየተ ኃጢአትን ፣ ቅድስናን ፣ አሸናፊነትን እና ይቅርታን ይሰጠን ዘንድ ሞታችንን ሞተ፤ የገባልንን ቃል ኪዳን ፈጸመ። “ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደ ነበረ፥ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል።” እንዲል። (ማቴ፲፪፥፵)
ጌታችን ከዐርብ ሠርክ እስከ እሑድ መንፈቀ ሌሊት ድረስ ሦስት ቀን ሦስት ሌሊት በመቃብር ዐርፏል። እነዚህ ቀንና ሌሊት የራሳቸው ትርጉም አላቸው። የነገረ ክርስቶስ መጽሐፍ ጸሐፊ መጋቤ ሐዲስ ክቡር ዶክተር ሮዳስ ታደሰ ስለ ሦስት ምክንያት እንደሆነ ይጠቅሳሉ: –
፩. ለአዳም ፣ ለሔዋን ፣ ለሕፃናቱ ሊክስ
፪. ለሥጋ ፣ ለነፍስ ፣ ለደመ ነፍስ ሊክስ
፫. ሞትን ፣ ፍዳን ፣ ኃጢአትን ሊያጠፋ ጌታችን ሦስት ቀን ሦስት ሌሊት በመቃብር ዐርፏል። (ነገረ ክርስቶስ፡ ገጽ፻፸፰)
ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት
ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ መቃብር ፫ ቀንና ፫ ሌሊት አደረ፡፡ ይኸውም ነቢዩ ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ እንዳደረው (ት/ዮና ፪÷፩-፪) ራሱም መድኀኔ ዓለም ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በ፫ ኛው ቀን አነሣዋለሁ ብሏል፡፡ (ዮሐ. ፪፥፲-፳፪) የተሰቀለ ዐርብ ፮ ሰዓት፤ ነፍሱን ከሥጋው የለየው ዐርብ ፱ ሰዓት ፤ ወደ መቃብር የወረደው ዐርብ ፲፩ ሰዓት ፤ የተነሣ ቅዳሜ ለእሐድ አጥቢያ ሌሊት ፮ ሰዓት ነው፡፡ ይህ ፫ ቀንና ፫ ሌሊት እንዴት ተባለ? ቢሉ የመጀመሪያው ብርሃኑን “ቀን” ጨለማውን “ሌሊት” በማለት የሚቆጠረው አቆጣጠር ነው፡፡ ይኸውም
ሦስቱ ቀኖች: –
🕕 ዐርብ ከነግህ/ጠዋት እስከ ቀን ፮ ሰዓት ብርሃን ነበር
🕘 ከ፱ ሰዓት እስከ ሰርክ ብርሃን ነበር
🕛 ቅዳሜ መዐልት/ቀን

  ሦስቱ ሌሊቶች: -

🕕 ዐርብ ከቀን ፮ ሰዓት እስከ ቀን ፱ ሰዓት አምላክ በመስቀል ላይ ሳለ ጨለማ ሆነ
🕛 ዐርብ ለቅዳሜ ሌሊት
🕛 ቅዳሜ ለእሁድ ሌሊት
ሌላው በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት ዓርብ ሌሊቱን እሑድ ቀኑን ይስቡና ይቆጠራል፡፡ 
ይኸውም: – ሌሊቶቹ
ሐሙስ ለዐርብ 
  ዐርብ ለቅዳሜ
  ቅዳሜ ለእሑድ
ቀኖቹ ደግሞ 
  ዐርብ ቀኑን
 ቅዳሜ ቀኑን
እሁድ ቀኑን ቆጥሮ ነው፡፡
ጌታችን ቀድሞ አዳምን፤ ሔዋንን ዐርብ ፈጥሮ ቅዳሜ እንዳረፈ ሁሉ አሁንም ያጡትን ገነትን ባጡበት ዐርብ ዕለት ሰጥቶ ቅዳሜ በመቃብር አርፎባታል ስለዚህም የተለየችቅዳሜናት።
➢ አራቱ ስያሜዎች፦
፩. ቀዳም ሥዑር
ሥዑር ማለት የግእዝ ግስ ሆኖ በአማርኛ የተሻረ ማለት ሲሆን በአንድ ላይ ሲነበብ የተሻረ_ቅዳሜ የሚል ትርጓሜ እናገኛለን። ምክንያቱ እንደ ቀደመቺቱ ሰንበት የማናርፍባት ይልቁንም ደቀመዛሙርቱን አብነት አድርገን በጾም በኀዘን ሕማሙን እያሰብንባት የምናሳልፋት ቀን በመሆኗ ቀዳም ሥዑር ተብላለች።
፪. ዐባይ ሰንበት
አምላካችን ሃያ ሁለቱን ሥነ ፍጥረት ፈጥሮ እንዳረፈባት የማዳኑንም ሥራ በመስቀል ላይ ፈጽሞ በአዲስ መቃብር ዐርፎ ውሎባታልና ዐባይ ሰንበት ተብላለች።
፫. ቅዱስ ቅዳሜ
በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን አድኖባታል ፣ ሲኦልን በዝብዟል ፣ ምርኮን ለራሱ ጨምሯል ፣ ዲያብሎስን አሳፍሯል ፣ የዕዳ ደብዳቤያችንን ደምስሷል ከሌሎች ቀናት ሁሉ የተለየች በመሆኗ ቅዱስ ቅዳሜ ተብላለች።
፬. ለምለም ቅዳሜ
በዚህ ዕለት በኖኅ ዘመን የጥፋቱ ውኃ ማለቁን የሰላም አብሣሪ ርግብ ለኖኅ ቄጤማ እንዳመጣችለት አሁንም የጥፋቱ ሞት ራቀልን ፣ ከሞት ወደ ሕይወት ተሸጋገርን ፣ አንቀጸ ገነት ተከፈተልን ሲሉ ካህናት አባቶቻችን የቅዳሜው የነግህ ጸሎት ከተጠናቀቀ በኋላ ለምእመኑ ለምለም ቄጤማ ስለሚሰጡ እኛ ምእመናንም በግንባራችን ላይ አድርገን ትንሣኤውን ስለምናከብር ለምለም ቅዳሜ ተብላለች።

ዐርብ ዕለተ ስቅለት

ከመምህር አዲሱ በዛብህ

ዕለተ ዓርብ በቤተክርስቲያን ልዩ ቀን ነው፡፡ የማይታመመው ታሞ የዋለበት፣ የወደቁ ከተረሱበት ከትቢያ የሚያነሳ እሱ ሲወድቅ ሲነሳ የዋለበት፣ ሕመምተኞችን የሚፈውስ እሱ ሲያቃስት የዋለበት፣ ከሲኦል የዲያብሎስ ግብር ነፃ የሚያወጣ ሲገረፍ የዋለበት፣ ወልደ እግዚአብሔር ለወዳጆቹ ድኅነት በመሥዋዕትነት ሙሽራ የሆነበት የደስታ ቀን፤ አሳዳጅ አሳሪያችን ዲያብሎስ ከነወጥመዱ ድል የተነሳበት ቀን ነው። ከዚህም የተነሳ በቤተክርስቲያን የተለያየ ምሥጢራዊ ስያሜዎች ተሰጥቶታል፡፡
የስቅለት ዓርብ ይባላል።
የዓለም ሁሉ መድኃኒት የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ ለዓለም ድኅነት መሥዋዕት ሆኖ የዋለበት ዕለት በመሆኑ የስቅለት ዓርብ ተብሏል። (ማቴ ፳፯፥፴፭)
መልካሙ ዓርብ ይባላል።
ይህም የሚያስገነዝበን ከስቅለተ ክርስቶስ በፊት ማንም ሰው ሲያጠፋ በመስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት ይደረግ ነበር፤ በተለይ በሮማውያንና በፈሪሳውያን ሕግ መስቀል የወንጀለኞች መቅጫ ነበረ። በዚህ ዕለት ግን ታሪክን የሚቀይር ነገርን የሚገለብጠው አምላክ የወንጀለኞች መቅጫ ምልክት የነበረውን መስቀል በደሙ ቀድሶ የምሕረት ምልክት፣ የሕይወት አርአያ፣ የዲያብሎስ ድል መንሻ ፣ የቤተክርስቲያን ጌጥ የገዳማት ዘውድ ስላደረገው እንዲሁም በዕለተ ዓርብ በሞቱ ሕይወትን ስላገኘን መልካሙ ዓርብ ተብሏል፡፡
➣ ጌታችን ከ፮-፱ ሰዓት በመስቀል ላይ ሳለ የተናገራቸው ፯ቱ ቃላት
፩ኛ. ኤሎሄ ኤሎሄ ኤልማስ ላማ ሰበቅታኒ፤ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ። (ማቴ. ፳፯፥፵፮)
፪ኛ. እውነት እውነት እልሃለሁ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትኖራለህ፡፡ (ሉቃ. ፳፫፥፵፫)
፫ኛ. አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ፡፡ (ሉቃ. ፳፫፥፵፮)
፬ኛ. አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው። (ሉቃ. ፳፫፥፴፬)
፭ኛ. እናትህ እነኋት፤ እነሆ ልጅሽ፤ (ዮሐ. ፲፱፥፳፮-፳፯)
፮ኛ. ተጠማሁ። (ዮሐ. ፲፱፥፴)
፯ኛ. ተፈጸመ ። (ዮሐ. ፲፱፥፴)
➣ ጌታችን ከ ፮-፱ ሰዓት በመስቀል ላይ ሳለ የተፈጸሙ ፯ቱ ተአምራት፤
፩ኛ. ፀሐይ ጨለመች።
፪ኛ. ጨረቃ ደም ሆነች።
፫ኛ. ከዋክብት ረገፉ።
፬ኛ. የቤተመቅደስ መጋረጃ ለሁለት ተከፈለ።
፭ኛ. ዐለቶች ተሰነጣጠቁ።
፮ኛ. መቃብራት ተከፈቱ።
፯ኛ. የሞቱት ተነሡ። (ማቴ. ፳፯፥፵፭-፵፮)
፭ቱ ቅንዋተ መስቀል ችንክሮች ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ እና ሮዳስ ይባላሉ።
➣ ሞትን ይሽረው ዘንድ የማይሞተው ሞተ፤ መከራንም ታገሰ።
➣ ሁሉን የያዘውን እርሱን ያዙት።
➣ ሁሉን የሚገዛውን እርሱን አምላካችንን እጅ አሰሩት።
➣ ሐጢአትን ይቅር የሚል እርሱን ሐጢአተኛ አሉት።
➣ የማይገረፍ አምላክ እርሱን የሰውን ሥጋ በመዋሐዱ ገረፉት።
➣ እንደ መብረቅ የሚያንፀባርቀውን ነጭ ልብስ የሚያለብስ አምላክ እርሱን ቀይ ግምጃ አለበሱት።
➣በእሳት በተጋረዱ ዙፋን ላይ የሚቀመጥ እርሱን በመዘባበቻ ወንበር ላይ አስቀመጡት።
➣እንደ ድንኳን ሰማይን የዘረጋ እርሱን በመስቀል ላይ ሰቀሉት።
➣የመላእክትን አለቆች በፊቱ በመፍራት የሚቆሙለት እርሱን በጲላጦስ ፊት አቆሙት።
➣በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈርድ እርሱን እንደበደለኛ ተፈረደበት።
➣አለምን ሁሉ በቅፅበት የፈጠረ እርሱ በመለኮቱ ሕያው ሆኖ በሥጋው ሞተ።
ጌታችን፣ መድኃኒታችን፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶ በሦስተኛው ቀን ሞትን ድል አድርጎ ተነስቶ ከኃጢአት ቁራኝነት፣ ከዲያብሎስ ባርነት ነፃ አውጥቶናል። እኛስ በሞቱ የዳንን ልጆቹ መንግሥቱን ለመውረስ ምን ልናደርግ ይገባናል?
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለእኛ መሞቱና መነሳቱ የመዳን መንገድን ከፍቶልናል፤ ነገር ግን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እኛም እርሱን አብነት ድርገን ያዘዘንን ሁሉ መፈጸም ይገባናል።
➣ ልናደርጋቸው የሚያስፈልጉን ነገሮች ፦
1.እምነት እና ንስሐ
በእግዚአብሔር በሙሉ ልብ ታምነን ከኃጢአታችን ልንጸጸትና ልንመለስ ይገባል። መጽሐፍ እንዲህ ይላልና፤ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ”። (ማቴ. ፫፥፩)
2. ቅዱስ ሥጋውን ክቢር ደሙን መቀበል
በጥምቀት (ከውኃና ከመንፈስ/ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና ከማኅጸነ ዮርዳኖስ) መወለድ “ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔርን መንግሥት ማየት አይችለም” (ዮሐ. ፫፥፫) እንዲል።
ቅዱስ ቁርባንን (ቅዱስ ሥጋናውን፣ ክቡር ደሙን) መቀበል ያስፈልጋል። “ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው” (ዮሐ. ፮፥፶፬) እንዲል።
3. ትእዛዛትን መጠበቅ
➣ እግዚአብሔርን በሙሉ ልብ መውደድ፤ “እግዚአብሔር አምላክህን በፍጹም ልብህ፥ በፍጹም ሰውነትህ፥ በፍጹም ኀይልህ፥ በፍጹም ዐሳብህ ውደደው፤” ። (ሉቃ. ፲፥፳፯ ፣ ዘሌዋ. ፲፱፥፲፰)
➣ ሰውን እንደ ራስ መውደድ፤ “ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ፤” (ዘሌዋ. ፲፱፥፲፰)
➣ ዐሥርቱ ትእዛዛትን መጠበቅ፤ “ብትወዱኝ ትእዛዛቴን ጠብቁ፤” (ዮሐ. ፲፭፥፲፬)
4. መጾምና መጸለይ
” ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስ ይሻልና፤ ሥጋ ግን ደካማ ነው” (ማቴ. ፳፮፥፵፩)
ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን ያስተማረን፣ አብነት የሆነን አምላክ ነውና በሁሉ ነገር እርሱን ልንመስለው ይገባናል። ̏ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና˝ (ዮሐ. ፲፫፥፲፭)
5. መልካም ሥራ መሥራት
በቅዱስ ወንጌል የተጻፈልንን በሕይወት መኖር አለብን።
ድሆችን መርዳት፣ የተራቡትን ማብላት፣ የተጠሙትን ማጠጣት ፣ የታረዙትን ማልበስ፣ … እነዚህንና የመሳሰሉትን የትሩፋት ሥራዎችን ልንተገብራቸው ያስፈልጋል። (ማቴ. ፳፭፥፥፴፩-፵፮)
➣ ምሕረትና ትሕትና መልበስ
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ የእጆቹ ፍጥረቶች አይሁድ ያን ሁሉ መከራ ሲያደርሱበት ጊዜ እፍ ብሎ ማጥፋት እየቻለ በዝምታ መከራውን ተቀብሏል፤ እንዲሁም በግፍ ለሰቀሉት አባት ሆይ የሚያደርጉትን ያውቁምና ይቅር በላቸው። (ዮሐ. ፲፱፥፩-፳፪) ፣ (ሉቃ. ፳፫፥፴፬)
6. ትዕግሥት እና ቅድስና
ፈተናን በእምነት መቋቋምና ራስን ከኃጢአት ማራቅ ያስፈልጋል።
“እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተ ቅዱሳን ሁኑ” (ዘሌዋ. ፲፱፥፪፣ ፩ኛ ጴጥ. ፩፥፲፭) እንዲል በቅድስና መንገድ ልንመላለስ ያስፈልጋል።
➣ በአጭሩ መንግሥተ ሰማያት በእምነት ብቻ ሳይሆን እምነት + ሥራ + ጸጋ የሚወረስ ነውና እምነትን ከምግባር ጋር አስተባብረን ልንይዘው ያስፈልጋል።
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር

ጸሎተ ኀሙስ

ከመምህር አዲሱ በዛብህ
ከስቅለትና ከትንሣኤ በፊት በሕማማት ሳምንት ያለው ሐሙስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ልዩ ልዩ ስያሜዎች አሉት፡፡ እነዚህንም ስያሜያት እንደሚከተለው እንመለከታለን።
ሀ. ጸሎተ ሐሙስ ይባላል።
የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ይለምን ይማልድ የነበረን ሥጋ የተዋሐደ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው መሆኑን ለማጠየቅ እንዲሁም ለአርአያነት ጠላቶቹ መጥተው እስኪዙት ድረስ ሲጸልይ በማደሩ ምክንያት ይህንን ስያሜ አገኘ። (ማቴ ፳፮፥፴፮-፵፮፣ ፲፯፥፩)
ለ. ሕጽበተ እግር ሐሙስ ይባላል።
ሕጽበተ እግር፦ ይህ ስያሜ የተሰጠው ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀመዛሙርቱን እግር በማጠቡ ምክንያት ነው፤ ይህም የሚያሳየው የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ መሆኑን ነው፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ካህናት በተለይም ሊቃነ ጳጳሳትና የደብር አስተዳዳሪዎች በመካከላችን ተገኝተህ የእኛንና የሕዝብህን ኃጢአት እጠብ ሲሉ ከአገልጋዮቹ ጀምረው በቤተክርስቲያን የተገኙትን ምእመናን እግር በወይንና በወይራ ቅጠል ሲያጥቡ ያረፍዳሉ፡፡
ሐ. የምሥጢር ቀን ይባላል።
ከሰባቱ ምሥጢራት አንዱ በዚህ ዕለት ተመሥርቷልና፤ ይኸውም ‹‹ይህ ስለእናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው፡፡ እንካችሁ ብሉ›› ጽዋውንም አንሥቶ አመሰገነ፤ ‹‹ይህ ስለእናንተ ነገ በመስቀል የሚፈስ ደሜ ነው ከእርሱ ጠጡ›› በማለት እኛ ከእርሱ ጋር፣ እርሱ ከእኛ ጋር አንድ የምንሆንበትን መንገድ ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ስያሜ ነው፡፡
በዚህ ዕለት ቅዳሴ ይቀደሳል፤ የሚቀደሰውም በለሆሳስ ሲሆን እንደ ቃጭል ሆኖ የሚያገለግለውም ጸናጽል ነው፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን ለመያዝ ሲመጡ ድምጻቸውን ዝቅ አድርገው፣ በለሆሳስ እየተነጋገሩ መምጣታቸውን ለማሰብ ነው፤ በቅዳሴውም ጸሎተ ተአምኖ፣ ኑዛዜ አይደረግም፤ ሥርዓተ ቁርባን ግን ይፈጸምበታል፤ ይህም ጌታችን የሰጠውን ዘለዓለማዊ ቃል-ኪዳን ለማሰብ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሓ ታጥቦ ተዘጋጅቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል ይኖርበታል፡፡
መ. የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል።
ጸሎተ ሐሙስ (የፋሲካ እራት) ፦ ምክንያቱም መሥዋዕተ ኦሪት ማለትም በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጐ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ነው፡፡ ‹‹ይህ ጽዋዕ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን ሐዲስ ኪዳን ነው፡፡ ከእርሱም ጠጡ›› በማለቱ ይታወቃል፡፡ (ሉቃ.22፥20) ኪዳን ማለት በሁለት ወገን መካከል የሚደረግ ውል፣ ስምምነት፣ መሐላ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ጌታችን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ዘለዓለማዊ ቃል-ኪዳን በራሱ ደም የፈጸመበት ዕለት መሆኑን በማሰብ የቃል-ኪዳኑ ፍጻሜዎች፣ ጠባቂዎች መሆን እንደሚገባን እንማራለን፡፡
ሠ. አረንጓዴ ሐሙስ ይባላል።
አምላካችን የጸለየበትን የአትክልት ቦታ ወይም ጌቴሴማኒ ለማሰብ ይህ ስያሜ ተሰጥቶታል።
ጌታ እንዴት፣ ምን እና ለምን ጸለየ?
እንዴት ጸለየ?
አምላካችን የምሥጢር ሐዋርያቱን (ዮሐንስ ፣ ያዕቆብ እና ጴጥሮስ) አምስት ትእዛዛትን (ተቀመጡ ፣ ትጉ ፣ ጸልዩ ፣ ተኙ ፣ ዕረፉ) በማዘዝ ግንባሩን ምድር አስነክቶ ሰግዶ ጸለየ።(ማቴ፳፮፥፴፮-፵፭)
ምን ጸለየ?
ሦስት ጊዜ ደጋግሞ የጸለየው ጸሎት አንድ ዓይነት ነው ይኸውም: – “አባቴ ቢቻልስ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፤ ነገር ግን አንተ እንደምትወድ ይሁን እንጂ እኔ እንደምወድ አይሁን አለ።” (ማቴ፳፮፥፴፮-፵፭)
ለምን ጸለየ?
፩. ምሣሌ ይሆነን ዘንድ ነው።
፪. ፈቃዱን ማስቀደም እንዳለብን እናውቅ ዘንድ ነው።
፫. ወደፈተና እንዳንገባ መጸለይ እንደሚገባ እናውቅ ዘንድ ሊያስተምረን ነው።
➣ የጸሎቱ ትርጓሜ ምንድ ነው?
፩. ዓለም እንድትድን እና ክብርን እንድታገኝ ለሞት ተላልፎ እንደሚሰጥ ገልጿል።
“ያለ እኔ ሞት የዓለሙ ድኅነት ያለ እኔ ሐሳር የዓለሙ ክብር አይቻልም እንጂ የሚቻልስ ከሆነ ይህ ጽዋዕ ሞት ይለፍልኝ። ነገር ግን ያንተ ፈቃድ ይደረግ እላለሁ እንጂ የእኔ ፈቃድ ይደረግ አልልም።” (ወንጌል አንድምታ ገጽ ፪፻፸፱)
፪. ሞት እንዲቀርልን እንደ ሞተ ገልጿል። “በእኔ ሞት የዓለም ድኅነት በእኔ ኃሣር የዓለም ክብር የሚቻልስ ከሆነ እኔ ከሞትሁላቸው ከእኔ ሞት የተነሳሣ ይህ ጽዋዕ ሞት ይቅርላቸው። (ወንጌል አንድምታ ገጽ፪፻፸፱)
፫. አብነት ይሆነን ዘንድ ሞትን እንደሚቀምስ ገልጿል። ” ከእኔ ለምዕመናን ይለፍላቸው ። እኔን አብነት አድርገው ይሙቱ ። ነገር ግን የእኔ ፈቃድ ካንተ ፈቃድ ልዩ ሁኖ የእኔ ፈቃድ ይሁን አልልም። የእኔ ፈቃድ ካንተ ፈቃድ ጋራ አንድ ነውና ያንተ ፈቃድ ይሁን እላለሁ እንጂ። ” (ወንጌል አንድምታ ገጽ፪፻፸፱)
➣ በዚህ ዕለት በወንጌላት የተመዘገቡ ድርጊቶችን ቀጥለን እንመልከት፦
ሀ. የፋሲካ ዝግጅት የተደረገበት ዕለት ነው።
ዝግጅቱ በሦስቱ ወንጌላት ላይ ተመዝግቧል፡፡ ማቴ. ፳፮፥፲፯-፲፱ ማር. ፲፬፥፩-፲፮፣ ሉቃ. ፳፪፥ ፮-፲፫)
ፋሲካ ማለት ማዕዶት ፣ መሻገር ፣ ማለፍ ማለት ነው፤ ይኸውም እሥራኤላውያን በግብጽ ምድር ሳሉ መልአኩን ልኮ እያንዳንዱ እሥራኤላዊ የበግ ጠቦት እንዲያርድና ደሙን በበሩ ወይንም በመቃኑ እንዲቀባ ለሙሴ ነገረው፤ ሙሴም ለሕዝቡ ነገረ፤ ሁሉም እንደታዘዙት ፈጸሙ፤ መቅሠፍት ከእግዚአብሔር ታዞ መልአኩ የደም ምልክት የሌለበትን የግብጻውያን ቤት በሞተ በኵር ሲመታ፤ የበጉ ደም የተቀባውን የእሥራኤላውያንን ቤት ምልክቱን እያየ ማለፉን ለማመልከት ነው፡፡ (ዘዳ.12፤1-13) በዚህ መነሻነት በየዓመቱ እሥራኤላውያን በመጀመሪያ ወራቸው በዐሥራ ዐራተኛው ቀን በግ እያረዱ የፋሲካን በዓል ያከብራሉ፡፡ ሀገራችንም አስቀድማ ብሉይ ኪዳንን የተቀበለች ሀገር እንደመሆኗ ይህ ድርጊት ይፈጸምባት ነበር፡፡ በአንጻሩም ዛሬ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ፋሲካ ተብሎ የተጠራበት ምክንያት በዚህ በፋሲካ በዓል ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ደሙን ስላፈሰሰልን ነው፡፡ በደሙ መፍሰስ ሞተ በኵር የተባለ ሞተ ነፍስ ቀርቶልናልና፤ ‹‹ፋሲካችንም ክርስቶስ ነው፡፡›› (1ኛቆሮ. ፭፥፮፣ 1ኛ ጴጥ. ፩፥፲)
ለ. በዚህ ዕለት እንደ ማክሰኞ ለደቀመዛሙርቱ ረጅም ትምህርት አስተምሯል።
ምሥጢረ ሥላሴ (የሦስትነት ትምህርት) ፤ ምሥጢረ ሥጋዌ (የአምላክ ሰው መሆን) ፤ (ዮሐ. ፲፬፥፲፮) የሚገኘው በጠቅላላ የዚህ ዕለት ትምህርት ነው፡፡ የትምህርቱም ዋና ዋና ክፍሎች ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንና የዳግም ምጽአቱ ነገር ነው፡፡ እነዚህም በስፋትና በጥልቀት መማር እንደሚገባ ሲያስረዳን በተአምራት ሊገልጥላቸው ሲችል በረጅም ትምህርት እንዲረዱት አድርጓል፡፡ ተማሪዎቹን እሱ እያስተማራቸው ሳለ ያልገባቸውን እየጠየቁ ተረድተዋል፡፡ ከዚህም እያንዳንዳችን በቤተክርስቲያን ተገኝተን መማርና ያልገባንን ጠይቆ መረዳት እንደሚገባን እንማራለን፡፡
ሐ. ይህ ዕለት ከደቀመዛሙርቱ አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታ ሆይ፣ መምህር ሆይ ብሎ በመሳም አሳልፎ የሰጠበት ዕለት ነዉ።
ጭፍሮቹም በዚሁ ዕለት ሌሊት የክብር ባለቤት የሆነውን ጌታችንን ይዘው ወደፊት፣ ወደኋላ እየጐተቱ፣ እያዳፉ ወደ ሊቀ ካህናቱ ወደ ቀያፋ ወስደውታል።
የመዝሙረ ዳዊት ምንባባት
በአንድ ሰዓት፡- “አፉ ከቅቤ ይልቅ ለዘበ፤ በልቡ ግን ሰልፍ ነበረ፤ ቃሎቹም ከዘይት ይልቅ ለሰለሱ፤ እነርሱ ግን እንደ ተመዘዘ ሰይፍ ናቸው” (መዝ፶፬፥፳፩)
በሦስት ሰዓት፡- “የጻድቅን ነፍስ ያደቡባታል፤ በንጹህ ደምም ይፈርዳሉ፡፡” (መዝ፺፫፥፳፩)
በስድስት ሠዓት፡- “የብዙ ሰዎችን ስድብ ሰምቻለሁና በዙሪያው ፍርሃት ነበረ በላዬ በአንድነት በተሰባሰቡ ጊዜ፤ ነፍሴን ለመንጠቅ ተሰባሰቡ፡፡” (መዝ ፴፥፲፫)
በዘጠኝ ሰዓት፡- “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፤ የሚያሳጣኝም የለም፤ በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፡፡” (መዝ. ፳፪፥ ፩-፪)
ኅጽበተ እግር፣ ሲጀመር ደግሞ “በሂሶጵ እርጨኝ እነጻማለው እጠበኝ ከበረዶም ይልቅ ነጭ እሆናለው፡፡” (መዝ ፶፥፯)
በመጽሐፈ ግብረ ሕማማት፡- “ከዚህ በኋላ የእግር እጥበት ሥርዓት ነው፤
ዲያቆን ሁለት ኲስኲስቶች ያቅርብ በውስጣቸውም ውኃ ይምላባቸው አንዱ ለእጅ መታጠቢያ እንዲሆን ካህኑም እስከ መጨረሻው ጸሎተ አኮቴት ይበል።
ጸሎተ ዕጣኑንም ደግሞ ዕጣንን ያሳርግ፤ ስለ ሰላም ስለ ሊቀ ጳጳሳት ስለ ማኅበር ይጸልይ፡፡ ሕዝቡም ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን ይበሉ፡፡ አቡነ ዘበሰማያትም ይበሉ ፤ ኀምሳኛውንም የዳዊትን መዝሙር ይበሉ፡፡” (ግብረ ሕማማት ገጽ ፭፻፵፪)
“ከዚህ በኋላ ሕዝቡ ይነሱ አርባ አንድ ጊዜ ኪራላይሶን ይበሉ፤ ካህኑም መስቀል ይዞ ውኃውን ሦስት ጊዜ አሐዱ አብ ቅዱስ (ልዩ ክቡር ንጹሕ ጽኑዕ ነው) ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ (ልዩ ክቡር ንጹሕ ጽኑዕ ነው) ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ (ልዩ ክቡር ንጹሕ ጽኑዕ ነው) እያለ ሦስት ጊዜ ውኃውን ይባርክ፡፡” (ግብረ ሕማማት ገጽ ፭፻፶፱)
“ከዚህ በኋላ ካህኑ እንደ ሥርዓቱ ኅጽበተ እግርን ያድርግ (ይፈጽም) ከዚህ በኋላም ጥቁር ልብስ ለብሰው ሥርዐተ ቅዳሴውን ይጀምሩ የቃጭል ድምጽንም አያሰሙ፡፡” (ግብረ ሕማማት ገጽ ፭፻፷፩)
በአሥራ አንድ ሰዓት፡- “በፊቴ ገበታን አዘጋጀህልኝ በጠላቶቼ ፊት ለፊት ራሴን በዘይት ቀባህ ጽዋዬም የተረፈ ነው” (መዝ. ፳፪፥ ፭-፮)
የአይሁድ ካህናት ያለበደል እና ያለጥፋት ንጹውን ክርስቶስን ለመስቀል ሞት እንዲደርስ በጭካኔ በዕለተ ሐሙስ ከሌሊቱ 3፡00 ጀምሮ ብዙ መከራ አደረሱበት እጅጉን ተሠቃየ፤ እያዳፉ አንዳች ሳይናገር አሠቃዩት ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ በትንቢት መነጽር የተመለከተውን የጌታችንን ሥቃይ እንዲህ ሲል ያመጣዋል፤
“ተጨነቀ፣ ተሠቃየም አፉንም አልከፈተም ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት በሸላቾቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ በማስጨነቅና በፍርድ ተወሰደ ስለ ሕዝቤ ኃጢአት ተመቶ ከሕያዋን ምድር እንደተወገደ ከትውልዱ ማን አስተዋለ? ከክፉዎቹም ጋር መቃብሩን አደረጉ…” እንዲል (ኢሳ፶፫፥፩-፰)
እንበለ ደዌ ወሕማም እንበለ ፃማ ወድካም አመ ከመ ዮም ያብጽሐነ ያብጽሕክሙ ለብርሃነ ትንሣኤሁ እግዚአብሔር በፍስሓ ወበሰላም አሜን! ፤ ያለ ደዌና ያለ ሕማም ያለ ፃማና ያለ ድካም እግዚአብሔር ለትንሣኤው ብርሃን እንደ ዛሬ ቀን በደስታና በፍቅር በአንድነት ያድርሰን ያድርሳችሁ አሜን!

ረቡዕ

ከመምህር ተሾመ ግዛው

እያንዳንዱ የሰሙነ ሕማማት ዕለታት ስያሜ እንዳላቸው ዕለተ ረቡዕም ራሱን የቸለ ምሥጢራዊና ታሪካዊ ትርጒም አለው፡፡ ይህም እንደሚከተለው በዝርዝርእንመለከታለን።
የምክር ቀን (ምክረ አይሁድ)
አይሁድ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስሰ ክርስቶስን የሚይዙበትን መንገድ ይፈልጉ ነበር፤ በመካከላቸው ምንም ዓይነት ልዩነት እንኳን ቢኖር ለኃጢአት ሥራ ግን ተባበሩ፡፡ ፰ት ለተለያየ አላማ የተቋቋመ ማኅበር (ስምንቱ ቤተ አይሁድ) ፦ ሊቃነ ካህናት፣ መገብተ ምኲራብ፣ ኃጥኣን መጸብሓን፣ ጸሓፍት ፈሪሳውያን፣ ሰዱቃውያን፣ ረበናት (መጽሓፈ ሰዓታት ንባቡና ትርጓሜው ሮዳስ ታደሰ ገጽ ፬፻፸፭)
ረበናት የሕዝቡን ሃይማኖታዊና ባሕላዊ ዕሤት ይጠብቃሉ ተብለው የተሾሙ ነበሩ፤ ነገር ግን ሕዝቡን ከመጥቀም ይልቅ የሚጎዳ ተግባር ላይ ተጠመዱ፤ ንጉስ ክርሰቶስን ለመስቀል በእለተ ረቡዕ ተማከሩ፤ ደሙም በላያቸው ላይ እንዲሆን በራሳቸው ላይ የሞት ፍርድን ፈረዱ። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እንደ ገለጸው ‹‹ማኀበራነ አይሁድ ተመድበሉ ለሰቂለ አምላክ ተማሐሉ፣ የአይሁድ ማኅበራት ተሰባሰቡ አምላክን ለመስቀል ተማማሉ›› ይች ዕለት የአዳም የመዳን ተስፋ፣ የነቢያት ትንቢታቸው ፍጻሜ እንዲያገኝ በቤተ አይሁድ ምክር የጸናበት እንዲሁም ለጨለማ አበጋዞች የኀዘን ዳራ የሰፋበት ነው፡፡
በዚህ ዕለት ጌታ ለሞት ተላልፎ እንዲሰጥ አይሁድ መክረው የተነሱበት አንዲሁም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእጃቸው የሚወድቅበት መንገድ ከይሁዳ ጋር ዘዴ የዘየዱበት ዕለት በመሆኑ የቤተ ክርስቲያነችን ሊቃውንት ዕለቱ ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዐመቱን ሙሉ በጾም እንዲታሰብ ሠርዓት ሠርተዋል።
የንስሓ ዕለት
ንስሓ ለሰው ልጅ ከበድል የሚነጻበት የነፍስ ሳሙና ነው፡፡ ቅዱሰ ኤፍሬም ሰለንስሓ እንዲህ ይለናል ‹‹ጌታ ሆይ ወርቅ ትሰጠኝ ዘንድ አለምንህም ወርቅ ክፉዎች የሚፈልጉት ንዋይ ነውና፡፡ ሀብትና ንብረትም አልለምንህም፤ እነርሱም ድኅነትን የሚያስገኙ አይደሉም፡፡ ይቅርታን ማግኘት ከወርቅ ይልቃል፡፡››
ጌታቾን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሠራቸው ድንቅ ሥራዎች ቅዱስ መጽሐፍ ማርያም ባለ ሽቶዋ በሚንቋትና ኃጢአተኛነቷን በየሄዱበት በሚመሰክሩባት ሴት ይቅርታን ያደረገበት ቀን ነው፡፡
ከቀናት ሁሉ ቅዱስ ተብለው የሚጠሩ ዕለታት ነፍስና ሥጋን የሚያነጹ ልዩ ዕለታቶች አሉ፡፡ ማርያም ለንስሓ የተነሳችበት ዕለት ከሌላው ጊዜ በተለየ ሁኔታ በኀዘንና በትካዜ የውስጧን ማንነት የሚያሳያትን በዓይነ ኅሊና ፊት እንጅ ለኃጢአትና ለበደል በሚያቆማት መስታወት ፊት ብቻ አልነበርም፡፡
ከዓይነ ሥጋ ዕይታ በመውጣት በዓይነ ኅሊና የታያት የክብር ዙፋን በመናፈቅ ውድና ክቡር የሆነ ሽቱ ፍለጋ ነበር የወጣችው፤ በወጣችበት ጊዜም ቀላል የማይባል ፈተና ገጥሟት ነበር፡፡ እርሱን ተቋቍማ ነገሥታት ይቀቡት የነበረውን እጅግ የከበረ ልዩ ሽቱ ፍለጋ ተንከራተተች፤ ፈልጋም ባገኘች ጊዜ በውድ ገንዘብ ገዛችው፡፡
የሽቱ ታሪክ በቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ይተረካል፡-
ሰባ ሰገል ለሕጻኑ የገበሩት ከጥንት አባቶቻቸው የመጣ ታሪክ እንዳለው ሁሉ ሽቱውም ልዩ ታሪክ አለው፡፡ ዳዊትና ሰሎሞን ይቀቡት የነበረዉ ውድ ሽቱ ሳይሆን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በወርኀ ስደቷ ጥጦስና ዳክርስ የተባሉ ሽፍቶች ነበሩ፤ እነዚህ ሽፍቶች የሕጻኑን ልብስና ጨማ ከዘረፉ በኋላ ፈያታዊ ዘየማን ሕጻኑን በመታቀፍ ሸኝቶት ነበር፤ የሕጻኑ ወዝም በሽፍታው ልብስ ይቀራል፤ ልዩ ጠረንም ነበረው፤ እንድታጥብለትም ለእናቱ ሲሰጣት ሽታው እስካሁን ከምታውቀው ሽቱ ሁሉ የተለየና በአንድ ተራ ሰው ቤት ሊገኝ የማገባው መሆኑን አውቃ ለነጋዴ ሸጠችው፤ ያ ነጋዴም የሚገዛው ሰው እስኪያገኝ ድረስ በልዩ ቦታ አስቀምጦት ነበር፤ ማርያም እንተ ዕፍረት በመጣች ጊዜ በውድ ዋጋ ሸጠላት፡፡
ማርያም እንተ ዕፍረት ይህንን የገዛችው ሽቱ ለክርሰቶስ እንዲገባ ዐውቃ የስምዖንን ዛቻና ግፊት ሳይበግራት በጽናት ተቋቍማ ወደ ክርስቶስ ቀርባ በፊቱ አቀረበችለት፡፡ በዐይኖቿም ዕንባ አፍሳ እግሮቹን አጠበችው፤ በዕንባዋ ያጠበችው እግሮቹም በጨርቅ ሳይሆን በውብ ፀጉሮቿ ነው እግሮቹን ያበሰችው፡፡
ያን ጊዜ ማርያም እንተ ዕፍረት በጌታ ዘንድ ከእንባዋ የተነሳ ይቅርታን አገኘች፤ ከበደል እስራትም ተፈታች፤ ከ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስትም ተቆጠረች፤ በቅዱሱ ዕለትም ቅድስናን ተቀበለች፡፡ (ሉቃ. ፯፥፴፯-፶)
ማርያም እንተ ዕፍረት እግዚብሔር የሰጣትን ውበትና መልክ ለቅድስና ሳይሆን ለኃጢአት አውላው ነበርና፤ ብዙዎቹ በእርሷ ውበት ተማርከው ገንዘባቸውን ጨረሱ፤ ትዳራቸውን አፈረሱ፤ ክቡር የሆነውንም የክርስቶስ ቤተ መቅደስ አረከሱ፤ በኃጢአት ዓለም እራሳቸውን አዋረዱ፤ ማርያም ግን ከዚህ ሁሉ ጥፋትና በደል በኋላ ወደ ቀልቧ ተመለሰች፤ ሁሉም ከንቱ መሆኑና በሚያልፈው ዓለም የማያልፈውን ክብር መግዛት ፈለገች፡፡
በማርያም እንተ ዕፍረት የሚከተሉትን የሕይወት ለውጥ እንመለከታለን፡-
ለኃጢአት ትጠቀመው የነበረውን መስታወት ለጽድቅ ማያ አደረገቸው፤
ለዝሙት ይውሉ የነበሩ ልብሶቿ ለክብር ሆኑ፤
ለዝሙት ይዘረጉ የነበሩ እጆች ለጽድቅ ተዘረጉ፤
ለዝሙት ይንበረከኩ የነበሩ እግሮቿ ለስግደት ተንበረከኩ፤
የጎልማሳ ቀልብን ሰብረው በመንገድ የሚያስቀሩ ዓይኖቿ የንስሓ እንባን አነቡ፤
ወደ ኃጢአት የእራት ግብዣ የሚገሰግሱ እግሮቿ ለክብር እንግድነት በቅድስና የእራት ግብዣ ቦታ ገሰገሱ፤
የጎልማሶች እጅ መንሻ በምትቀበልበት እጆቿ የተለየ ሽቱ ለነገሥታት እንደሚገባው ንጉሠ ነገሥት ለሆነው ለክርስቶስ አቀረበች፡፡
ይህች ዕለት ለእርሷ የተቀደሰ ሐሳብን ያሰበችበት፣ ያባከነችውን ጊዜ የምትክስበት፣ ለኃጢአት መኳኳል ትጠቀምበት የነበረውን ጊዜ ለጽድቅ ያደረገችበት ቅዱስ ዕለት፤ ከዓለም ሁካታና ጩኸት የተለየችበት ቅድስት እለት ናት፡፡
ዛሬ እኛ ከነበርንበት ውደቀት ለመውጣት ብዙ ምክንያች እንደረድራለን ያለንበትን ቦታና በዙሪያችን ያሉ ሰዎችን ከውደቀታችንም ላለመነሳት ምክንያት እናደርጋቸዋለን፡፡ ከዚህች ብርቱና ቆራጥ ሴት የምንማረው ለበጎ ተግባር ቁርጥ ውሳኔ መወሰንና ፈጥኖ በተግባር ማዋልን ነው። ያኔ ታላቅ የሕይወት ለውጥ በኑሯችን ይከሰታል።
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን

ሰሙነ ሕማማት ሠሉስ

ከመምህር ተፈሪ መንገሻ

በኢ.ኦ.ተ.ቤ/ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት የሰሙነ ሕማማት ዕለታት የየራሳቸው ስያሜና ምሥጢር አላቸው። ከእነዚያ መካከል ዕለተ ሠሉስ የትምህርት ቀን የጥያቄ ቀን በመባል ይታወቃል።

ይህንንም አስመልክቶ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በዕለቱ ጌታ ረጅም ትምህርት ያስተማረበትና ከአይሁድ፣ ከጸሓፍትና ከፈሪሳውያን ብዙ የተንኮል ጥያቄዎችን ተቀብሎ ለእነርሱም በጥበብ መልስ የሰጠበትን ድንቅ ትምህርት ሥርዓት ሠርታ ትዘክራለች/ታስታውሳለች። ይህች ዕለት የሰው ልጅ ውሱን በሆነው አዕምሮውና በተንኮል በተሞላው ልቡ ጥበብንና እውነትን (ክርስቶስን) ሊፈትን የሞከረበትና ጥበብ ክርስቶስ ግን ጥያቄአቸውን በጥያቄ የረታበት፣ ሐሰታቸውን የገለጠበት ዕለት ነው።

በሰኞ ዕለት ነጋዴዎችን ከቤተ መቅደሱ በማስወጣት ስላነጻ፣ ስለገሠጸ በማግሥቱ ማክሰኞ ዕለት ይህንን በማን ሥልጣን እንደሚያደርገውና ሌሎች ብዙ ጥያቄዎችን ጠይቀውታል። (ሉቃ. ፲፥፵፭)

በእነዚህ ጥያቄዎች ውስጥ ብዙ ጥልቅ ምሥጢራትን የያዘ ክፍል ነውና እነርሱን በዝርዝር ከፋፍለን እንደሚከተለው እንዳስሳቸዋለን።

ተንኮል በጥበብ ፊት (ሉቃ. ፳፥፩-፰)

በሰኞ ዕለት ጌታችን ቤተ መቅደሱን ከነጋዴዎች ማጽዳቱና የሃይማኖቱን ሥርዓት ወደ ንግድ የለወጡትን ማስወጣቱ (ሉቃ. ፲፱፥፵፭) በቤተ መቅደሱ ላይ የበላይነት አለን የሚሉት የካህናት አለቆችና ጸሐፍት በእነርሱ ዘንድ “የጥቅም መነካት” ፈጥሮባቸው ነበር።

በነጋታው በዕለተ ሠሉስ ጌታችን በቤተ መቅደስ እያስተማረና ወንጌልን እየሰበከ ሳለ፣ እነዚህ መሪዎች ከሽማግሌዎች ሆነው በመምጣት ድንገተኛ “የሥልጣን ጥያቄ” አቀረቡ።

“ወይቤልዎ፥ ንግረነ በመባሕተ መኑ ትገብር ዘንተ? ወመኑ አብሐከ ትግበር ከመዝ? ንገረን ይህንን በምን ሥልጣን ታደርጋለህ? ወይስ ይህን ሥልጣን የሰጠህ ማነው? አሉት” (ሉቃ. ፳፥፪)

ይህንንም ሲሉ የሥልጣኑን ምንጭ፣ “የማድረግ መብት” ወይም “ሕጋዊ ፈቃድ” ማለታቸው ነው። እነርሱ ጌታችንን የጠየቁት እንደ አምላክ ሳይሆን “እኛ ካልሾምንህ፣ እኛ ካልፈቀድንልህ ቤተ መቅደሱን የማጽዳት መብት ከየት አገኘህ?” የሚል ለአንድ ሰው የሚጠየቅ በዘመኑ ቋንቋ የቢሮክራሲ ጥያቄ ነው።

ክፋት ልባቸውን ስላሳወረው በዓይናቸው የሚመለከቷቸውን ተአምራት አይቶ ከማመን ይልቅ ከባለሥልጣን የፈቃድ ወረቀት ጠየቁት። ለስሕተታቸው እውነተኛ ማስረጃ ማቅረብ ስለማይችሉ ይህንን ስሕተታቸውን የገለጠባቸውን እውነት ከመቀበል ይልቅ መለኮታዊውን እውነት በሰዋዊ ሥርዓት ለመለካት ሞከሩ።

ዛሬም በሕይወታችን ውስጥ እውነትና ቅድስና ሲመጣ ቀድሞ የሚቃወመን የልባችን ክፋት ጥቅመኝነት ነው። ሀገራችንንና ዓለማችንን ብሎም ቤተ ክርስቲያናችንን እየፈተነ ያለው ከእውነት መንገድ ይልቅ በሐሰት የተገነባ ዝና፣ ስግብግብነትና ሆዳምነት ነው።

በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በኑሯችን የአንድን ሰው መንፈሳዊ ፍሬ ከመመልከት ይልቅ፣ “ከየት መጣ? ማን ፈቀደለት? የእኛ ወገን ነውን? በሚል ሥጋዊ ቅናት የእግዚአብሔርን ሥራ እንቃወማለን።

ጸሐፍት ይህ መንፈሳዊ ውድቀታቸው ሳያንስ እውነትን ለመሸፈን ያደረጉት ጥረት ይደንቃል። ይህ ጥያቄያቸው በተንኮል የተሞላና በሁለት አማራጮች መካከል አጣብቂኝ ውስጥ የሚከት ጥያቄ ነበር።

➜ ሥልጣኔ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ቢል፦ አንተ ራስህን አምላክ አድርገሀል ብለው ሊከስሱት ነው።

➜ ሥልጣኔ ከሰው ዘንድ ነው ቢል፦ “እንግዲህ ተራ ሰው ከሆንክ እንዲህ ያለውን ታላቅ ድርጊት የማድረግ መብት የለህም” ብለው በሕዝብ ፊት ሊከሱትና ሊያስሩት ዐቅደው ነበር።

ጌታችን ግን የእነርሱን ተንኮል ተረድቶ መልሱን በጥያቄ መለሰላቸው።

➜ “ጥምቀቱ ለዮሐንስ እምአይቴኑ ይእቲ እምሰማይኒ ወሚመ እምሰብእኑ፣ የዮሐንስ ጥምቀት ከሰማይ ነበረችን ወይስ ከሰው? አላቸው።” (ሉቃ. ፳፥፬)

ይህ የጌታ ጥያቄ ጠያቂዎችን በራሳቸው ጥያቄ ወጥመድ ውስጥ የሚከት ጥያቄ ነበር። ጌታ እነርሱ ሊያጠምዱበት ከዘረጉት ወጥመድ አልፎ እነርሱን በጥያቄ አጠመዳቸው። እነርሱ ባሰቡበት መንገድ አለመመለሱ ብቻ ሳይሆን እነርሱን አጣብቂኝ ውስጥ የሚከታቸው የመልስ ጥያቄ ሆነባቸው። ስለ እርሱ ማንነት በራሳቸው አንደበት እንዲመልሱ የሚያደርግ ጥያቄ ነበር።

ጌታችን ዮሐንስ መጥምቅን ጠቅሶ የጠየቃቸው ለምንድነው? ቢሉ

➜ ዮሐንስ መጥምቅ ስለ ክርስቶስ “እነሆ የእግዚአብሔር በግ” (ዮሐ.፩፥፳፱) ብሎ መስክሯልና ነው።

ስለዚህ እነርሱም “ከሰማይ ናት” ካልን፦ የዮሐንስን ምስክርነት መቀበልና በክርስቶስ ማመን ነበረባቸሁ ሊለን ነው። “ከሰው ናት” ካልን ደግሞ ሕዝቡ ዮሐንስን እንደነቢይ ስለሚያከብሩት ሕዝቡን በመፍራት በሁለት የአጣብቂኝ መልስ ውስጥ ገቡ።(ሉቃ. ፳፥፭-፮)

እግዚአብሔርን ብዙ ጊዜ “ለምን እንዲህ ሆነብኝ?” ብለን ስንጠይቅ፣ እርሱ ደግሞ “ቀድሞ የሰጠሁህን ጸጋ ምን አደረግከው?” ይለናል። (ማቴ.፳፭፥፲፭)

ጌታ እዚህ ጋር እያሳየን ያለው እውነትን ፍለጋ ወደ ውጭ ከመሄዳችን በፊት ወደ ውስጣችን እንድንመለከት ነው። ብዙ ጊዜ መልሱ እጃችን ላይ እያለ እኛ ግን እግዚአብሔርን “ሥልጣንህን አሳይ” እንለዋለን።

➜ በልባቸው ላይ ሐሰትን ያነገሡና እውነትን መቀበል የተሳናቸው ጸሐፍት ለጌታ ጥያቄ በቀጥታ ከመመለስ ይልቅ እውነቱን እያወቁ እንዳላወቁ ሆነው “መልሰውም፦ ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም አሉት።” (ሉቃ. ፳፥፯)

➜ “አናውቅም” የሚለው መልሳቸው በታሪክ ውስጥ እጅግ አሳፋሪ ውሸት ነው። እውነቱን ስለማያውቁ ሳይሆን ማወቅ ስለማይፈልጉ ነውና። “ከሰማይ ብንል….ከሰው ብንል….” እያሉ የሚያሰሉት ስለ እውነት ሳይሆን ስለ ጥቅማቸውና ስለ ደኅንነታቸው ነበር።

ዛሬም በዘመናችን “አናውቅም” ባዮች በዝተዋል። በሀገራችን፣ በቤ/ክ አገልግሎታችንና አጠቃላይ በማኅበራዊ ሕይወታችን እውነት ሲገለጥና ግፍ ሲሠራ እያየን፣ ጥቅማችን እንዳይነካ “አላየሁም፣ አልሰማሁም፣ አናውቅም” እንላለን።  “ብርሃን ወደ ዓለም መጣ፣ ሰዎች ግን ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ወደዱ” እንዲል ቅዱስ ዮሐንስ። (ዮሐ. ፫፥፲፱)

➜ “ኢየሱስም፦ እኔም በምን ሥልጣን እነዚህን እንዳደርግ አልነግራችሁም አላቸው።” (ሉቃ. ፳፥፰)

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህንን የጌታ መልስ ሲተረጉም ጌታ መልስ የከለከላቸው ሊቀበሉት ዝግጁ ስላልሆኑና ለእሪያ ዕንቁ ስለማይጣል መሆኑን ይናገራል። (ማቴ. ፯፥፮)

ሰው በልቡ ክፋትን፣ ቂምንና ተንኮልን ሸምቆ የሚጸልየው ጸሎት መልሱ ዝምታ ነው። “በልቤስ በደልን አይቼ ብሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር።” (መዝሙር ፷፯፥፲፰) በማለት ነቢዩ ዳዊት እንደተናገረ፡፡

ስለዚህ እኛም፡-

➜የእግዚአብሔርን ሥራ በራሳችን አእምሮ አንመዝን። “ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና” (፩ኛ ቆሮ.፩፥፳፭)

➜ ለእውነት ታማኝ እንሁን። እንደ ጸሐፍት በሰዎች ዘንድ የሚመጣብንን “ውግረት፣ ይሉኝታን፣ መገፋትና ሞትን ወዘተ ፈርተን እውነትን መካድ አይገባንም። እንደ ዳዊት “እስመ ለልየ አአምር ጌጋይየ ወኃጢአትየኒ ቅድሜየ ውእቱ በኵሉ ጊዜ፤ እኔ መተላለፌን (በደሌን) አውቃለሁና፥ ኃጢአቴም ሁልጊዜ በፊቴ ነውና።” (መዝ.፶፩፥፫) ብለን እውነት ሐሰትን እንዲያሸንፍ በፊቱ ለንስሐ መቅረብና ማልቀስ አለብን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር፤ ወለወላዲቱ ድንግል፤ ወለመስቀሉ ክቡር

የጥያቄ ቀን

ከኄራኒ ጠና

ጥያቄ ቀን

 ለፍጥረተ ዓለም ሶስተኛ ቀን የሆነችው ማክሰኞ በህማማት ሳምንት የጥያቄ/ የትምህርት ቀን ተሰኝታ፤ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀድሞ በተናገረውና ባደረገው ላይ አይሁድ ጥያቄ ማቅረባቸው እንዲሁም እርሱ መልስ በመስጠት ማስተማሩ ይዘከርባታል።

  • ጥያቄ

 ዕለቱን የጥያቄ ቀን ያሰኘው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ሰኑይ ያደረገውን አንጽሆተ ቤተ መቅደስ ተከትሎ ጸሐፍትና ፈሪሳውያን ይህንን ገበያ መፍታት፤ ተአምራትን ማድረግ ፤ ከምድራውያን ነገስታት ከሌዋውያን ካህናት ያይደለ ትምህርት ማስተማርን በምን ስልጣን ታደርገለህ? ይህንንስ ስልጣን ማን ሰጠህ? ሲሉ መጠየቃቸው ነው። (ማቴ ፳፩፥ ፳፫ – ፳፯)

ጸሐፍት እና ፈሪሳውያን ክርስቶስ ይህንን በማን ስልጣን አንደሚያደርግ ጠፍቷቸው አልነበረም ለጥያቄ የመጡት፤ ይልቁንም እርሱን ለመፈታተን እና ከቃሉም ስሕተትን ለማግኘት ነበር። ልቡና እና ኩላሊትን የሚመረምር ሁሉን አዋቂ አምላክ ግን የልባቸውን ጠማማ መሻት ቀድሞው አውቆ ነበርና ጥያቄያቸውን በሌላ ጥያቄ መለሰላቸው።

“ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ ደግሞ አንዲት ነገር እጠይቃችኋለሁ እናንተም ያችን ብትነግሩኝ እኔ ደግሞ እነዚህን በምን ሥልጣን እንዳደርግ እነግራችኋለሁ የዮሐንስ ጥምቀት ከወዴት ነበረች ከሰማይን ወይስ ከሰው አላቸው። እነርሱም እርስ በርሳቸው ሲነጋገሩ፦ ከሰማይ ብንል፦ እንኪያስ ስለ ምን አላመናችሁበትም ይለናል ከሰው ግን ብንል ዮሐንስን ሁሉም እንደ ነቢይ ያዩታልና ሕዝቡን እንፈራለን አሉ። ለኢየሱስም መልሰው፦ አናውቅም አሉት። እርሱም ደግሞ፦ እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንዳደርግ አልነግራችኹም አላቸው።” 

እነርሱ በሰው ዘንድ መከበሩን የቃሉ ትምህርትን መወደዱን አይተው ለማወቅ በቅንነት በመጠየቅ ፋንታ በቅናት ምን ብንለው እናሳጣዋለን ወጥመዳችን ውስጥ እናስገባዋለን ብለው አውጥተው አውርደው ጥያቄዎቻቸውን ይዘው መጡ ስለዚህም እንደ አመጣጣቸው መለሰላቸው።

እኛስ ዛሬ ምን ዓይነት ጥያቄ ይዘን ነው ወደ አምላካችን ብሎም ወደመምህራኖቻችን የምንቀርበው? በልባችን ክፉ ምኞትን ይዘን በንግግራችን ዋሽተንበት እንዳይሆን እንጠንቀቅ (ገላ ፮፥፯) በንፁሕ እና በተሰበረ ልብ ነው አምላካችን ፊት መቅረብ ያለብን እንጂ እንደ ጸሐፍት እና እንደ ፈሪሳውያን ነገር ጐንጕነን ሊሆን አይገባም፤ ስንጠይቅ አውቀን ለመራቀቅም አይሁን ይልቁንም በሕይወት ለመኖር እንጠይቅ፤ አዋቂ ነው/ናት ለመባል ለትዕቢትም አይሁን/ ለመረዳት እንጂ፤ የሰውን ስህተት ለማጕላትና ለመሰናክል አይሁን፤ እንዳጠቃላይ ከእርሿቸው መጠበቅ እንዳለብን አምላክ ነግሮናልና ልጠነቀቅ ይገባናል።

  •  ምሳሌዎች

 ክርስቶስ ጥያቄያቸውን በዚህ መንገድ ካስተናገደ በኋላ በምሳሌ ያስተምራቸው ጀመር ሁለት ምሳሌዎችንም ነገራቸው።

 ምሳሌ አንድ: – ፪ ልጆች የነበሩት አንድ ሰው ነበረ፤ ወደ አንደኛው ልጁም ሄዶ ልጄ ሆይ በወይን አትክልቴ ሥራ አለው፤ እርሱም ሊሠራ አልወደደም፤ ኋላ ተመልሶ ግን ተጸጸተ ሠራም፤ አባትየው ወደ ሌላኛው ልጁ አቀና እንዲህም አለው፤ ሌላኛውም ልጅ እሺ አለ አልሰራም ከሁለቱ የአባቱን ፈቃድ የፈጸመው ማን ነው? አላቸው። እነርሱም የፊተኛው አሉት።

 በዚህ ምሳሌ አባት የተሰኘው እግዚአብሔር ሲሆን፤ የመጀመሪያው ልጅ ደግሞ በንስሐ የተመለሱ ቀራጮችን ይወክላል፤ ሁለተኛው ልጅ ደግሞ ጸሐፍትና ፈሪሳውያንን ይወክላል። ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ይህንን ሲያብራራ እግዚአብሔር ከንግግራችን ይልቅ ሥራችንን እንደሚፈልግ ይነግረናል፤ ንግግራቸውን ካቀኑ መልካሙን ቃል ከሚናገሩ ነገር ግን በግብራቸው ከሚበድሉ፤ ክርስቶስም ራሱ “ስለዚህ ያዘዟችሁን ሁሉ አድርጉ ጠብቁትም ነገር ግን እየተናገሩ አያደርጉትምና እንደ ሥራቸው አታድርጉ” (ማቴ ፳፫፥፫) ካላቸው ጸሐፍትና ፈሪሳውያን ቀድመው በቀደመ ሕይወታቸው ያላመኑ እንዲሁም የበደሉ ነገር ግን በንስሐ የተመለሱ ቀራጮች መንግሥቱን ይወርሳሉ አለ። እኛ አሁንም ከዚህ ምሳሌ እኒህን እንማራለን: –

  1.  የአንደበት ብቻ ሳይሆን የተግባርም ክርስቲያን ልንሆን እንደሚገባ

ውጫዊ በሆነው ሰው በሚያየው በመድረክና በማህበራዊ ሚዲያ ስለ እምነታችን መመስከር ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር በሚያየው ሰው በማያየው የግል ሕይወታችንም መልካሙን ምግባር ልንሠራ ይገባናል። ይህም ያለንን እውቀት፣ ገንዘብ የመሳሰሉትን ለተቸገሩ በመመጽወት ፤ በፍጹም ትሕትና እና ፍቅር ከሁሉ ጋር በመኖር…. ሊገለጽ ይችላል።

  •  አሁን አንዳልረፈደ

ልክ እንደቀራጮች ለእግዚአብሔር እምቢ ያልንባቸው ከሕጉም ያፈነገጥንባቸው ጊዜያት ቢኖሩም የምሕረት አባት የሆነው አምላካችን በንስሐ ሊቀበልን ከመንጋውም ሊቀላቅለን የታመነ ነውና፤ ኑ ዛሬ ነገ ሳንል በንስሐ ወደ አምላካችን እንመለስ።

 ምሳሌ 2: –

‹‹ባለቤት ሰው ወይንን ተከለ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፤ መጭመቂያም አስቈፈረለት፤ ግንብም ሠራለት፤ ለገባሮችም ሰጥቶአቸው ሄደ፡፡ የሚያፈራበት ወራት በደረሰ ጊዜም፥ ከወይኑ ፍሬ ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮችን ወደ ገባሮቹ ላከ፡፡ ገባሮቹም አገልጋዮቹን ይዘው፥ አንዱን በበትር ደበደቡት፤ አንዱንም ገደሉት፤ ሌላውንም በድንጋይ መቱት፡፡ ከዚያም በኋላ ከቀደሙት የሚበዙ ሌሎች አገልጋዮችን ላከ፤ እነርሱንም እንዲሁ አደረጉባቸው፡፡ በኋላም ልጄንስ ይፈሩት ይሆናል ብሎ ልጁን ላከ፡፡ ገባሮቹም ልጁን ባዩት ጊዜ እርስ በርሳቸው፡- እነሆ፥ ወራሹ ይህ ነው፤ ኑ እንግደለውና ርስቱን እንውረስ ተባባሉ፡፡ ይዘውም ከወይኑ ቦታ ወደ ውጭ አውጥተው ገደሉት፡፡›› (ማቴ ፳፩ ፥፴፫-፴፱)

በዚህም የምሳሌ ትምህርት የመሬቱ ባለቤት እግዚአብሔር አብ ሲሆን፤ ግንብ፣ ቅጥር እና መጭመቂያ የተሰኙት ደግሞ መቅደሱ፣ የኦሪት ሕግና መሰዊያው ነበሩ፤ ገበሬዎች ደግሞ የአይሁድ ካህናትና አባቶች ናቸው፤ ሰራተኞቹ የተባሉት በየዘመናቱ የተላኩ ነብያት ሲሆኑ፤ የተወደደው ልጅም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

ጌታችን በዚህ ምሳሌ የተናገረው በአጭሩ ከብሉይ ወደ ሐዲስ ኪዳን የተደረገውን ሽግግር ነው። እግዚአብሔር የወይን አትክልት ስፍራ ለተባለችው ለእስራኤል እና ለተመረጠው ሕዝቧ በየዘመኑ ነብያትን ልኮ እንዳስተማራቸው፤ እነርሱም በነብያቱ መከራን እንዳጸኑባቸውና እንደገደሏቸው ይህንንም እየተመለከተ ስለ ምሕረቱ ብዛት በድጋሚ ነብያቱን እንደላከ መልሰውም ያንኑ እንዳደረጉባቸው ከዚያም በመጨረሻው የሚወደውን አንዱን ልጁ የተባለው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደላከ በእርሱም እንዳላመኑበት ይልቁንም  በእንጨት መስቀል እንደሰቀሉት ያሳየናል።

ይህም በውጤቱ የወይኑ ስፍራ በክርስቶስ ካላመኑት አይሁዳውያን ተወስዶ ለአዲሶቹ ገበሬዎች በክርስቶስ ላመኑት ለአሕዛብ መሰጠቱን እና ሐዋርያዊ የሆነች ቤተክርስቲያን መመሥረቷን ያሳየናል።

 ከዚህም ምሳሌ እኛ የሚከተሉትን ልንማር ይገባናል: –

  1.  በቤተ ክርስቲያን ያለን ስልጣን ለብቻው ለድኅነታችን ዋስትና እንደማይሆን፤

በምሳሌው ገበሬ የተሰኙት የአይሁድ መንፈሳዊ መሪዎች ካህናት የነበራቸው ስልጣን አላዳናቸውም፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ከእነርሱ የጠበቀውን መልካሙን የምግባር ፍሬ አላፈሩምና። አሁንም እኛ ምንም እንኳ በመድረክ ብንዘምር ስነ-መለኮት አዋቂ ነን ብንል መልካሙን ፍሬ ትሕትናን፣ ፍቅርን ፣ መታዘዝን ገንዘብ ካላደረግን እኒህ ለእኛ ምንም ጥቅም እንደማይሰጡን ነው።

  •  ክርስቶስን መካድ የክሕደት ሁሉ መጨረሻው እንደሆነ

 አይሁድ ልጁ ወራሹ መጣ እርሱን ብንገድል ውርሱን እንወስዳለን ብለው እንዳሉትም አደረጉ፤ ያን ጊዜም ሁሉን ነገር አጡ። እኛም ዛሬ በስሕተት ትምህርት ተወስደን ክርስቶስን እንደ አምላክነቱ ባንቀበለው እንደ አይሁድ ሁሉን እናጣለን። በአገልግሎታችንም ሆነ ከሁሉም ነገር በፊት የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት እና ጌትነቱን በፍጹም ልብ ልናምን ይገባናል። የሐዲስ ኪዳኗ ሐዋርያዊት ቤተክርስቲያንም በዚህ እውነት ላይ ተመስረታለችና። (ማቴ ፲፮ ፥ ፲፰)

  •  የአሁኑ ገበሬዎች እኛ ነን!

 የወይን ቦታው አሁን ለሌላ ፍሬውን ለሚያፈሩ ገበሬዎች ተሰጥቷል፤ ሌሎቹ ገበሬ የተሰኘችው የሐዲሷ ቤተ ክርስቲያን ኅብረት ናት፤ ያህ ማለት እኔ፣ አንተ፣ አንቺ ሁላችንም የቤተክርስቲያን አባላት ማለት ነን። ታዲያ እኛ እውነት ፍሬ እያፈራን ነውን? እኛ የወይን ፍሬው ባለ አደራዎች እንጂ ባለቤቶች አይደለም፤ እናም ባለቤቱ መጥቶ በሰጠኋችሁ ሃይማኖት ሕግ እና ሥርዓት ምን መልካም ፍሬ አፈራችሁ? ቢለን የምንመልሰው አዘጋጀተናልን? ለዚህም ነው በየቀኑ ራሳችንን ለእግዚአብሔር መንግሥት የሚሆን ምን ፍሬን እያፈራን እንደሆነ ልንጠይቅና በማስተዋልም ልንኖር የሚገባል።

  •  ትምህርት

 በዕለተ ሠሉስ ከላይ ከተነጋገርነው ከጸሐፍት፣ ከፈሪሳውያን እና የጌታችን መልስ ባሻገር ክርስቶስ በቤተ መቅደስ ያስተማረው ረጅም ትምህርትም ታስቦ ይውላል። (ሉቃ ፳፩፥፪-፴፮)

በዚህም ጌታችን በመጀመሪያ የመበለቲቱ ሁለት ሳንቲም መባእ አመስግኗል፤ በዚያ ብዙ ወርቅ እና ሌላ ውድ የሆነ መባን የሚያገቡ ብዙዎች እያሉ ለምን የእርሷን ሁለት ሳንቲም መባእ አመሰገነ? ቢሉ ሌሎቹ ትርፍና ኪሳራቸውን አስልተው ሲሰጡ እርሷ ግን ያላትን ያለስስት ሰጥታለችና። የአቤልን መሥዋዕት የወደደ ያው እግዚአብሔር አሁንም ከስጦታው ብዛት ይልቅ የልቧን ንጽሕናና ከጎዶሎዋ ላይ ሳትሰስት መስጠቷን አደነቀ።

ጌታችን ዛሬም ቢሆን ያንኑ ስጦታ ይወዳል፤ ያለን ሁሉ ከእርሱ ነውና ለእርሱ ክብር ልናውለውም ይገባል አምላካችን እኮ አይደለም ብርና ንብረት ሕይወትም የሚሰጠው ነው ይህንንም እንኳ ብናደርግ እርሱ ካደረገልን ጥቂቱን እንኳን አንመልስም።

ከዚህም በተጨማሪ በዚህች እለት አምላካችን ስለ ዳግም ምጽአቱ እና ከእርሱ በፊት ስለሚፈጠሩት ነገሮች ከቤተ መቅደሱ መፍረስ ጋር አያይዞ በሰፊው አስተምሯል። ይህንንም ብቻ ተናግሮ ዝም አላለም፤ ምን ልናደርግ እንደሚገባንም ‹‹ራሳችሁን ጠብቁ፤ በመብልና በመጠጥ፥ በመቀማጠልና የዓለምን ኑሮ በማሰብ ልባችሁን አታደንድኑ፤ ያቺ ቀንም በድንገት ትደርስባችኋለች፡፡ በምድር በሚኖሩት ሁሉ ላይ እንደተዘረጋች ወጥመድ ትደርሳለችና፡፡ እንግዲህ ከዚህ ከሚመጣው ሁሉ በጸሎታችሁ ማምለጥ እንድትችሉ፥ በሰው ልጅ ፊትም እንድትቆሙ ሁልጊዜ ትጉ፡፡›› (ሉቃ ፳፩፥፴፬-፴፮) ሲል ነግሮናል። እኛም በዳግም ምጽዓቱ የምናምን ይህንን በማሰብ ማስታዋል እንኑር!

በአጠቃላይ በዚች የሰሙነ ሕማማት ማክሰኞ የአይሁድን ጥያቄ እና የጌታችንን ትምህርት አስበን እንውላለን። ከሁሉ በላይ በዕለቱ የሚነገረውን የእግዚአብሔር ቃል እንደ ሕይወታችን ስንቅ ልንወስደው ይገባናል። ካስተማሩት ብዙ እንደሚጠብቁበት ጌታችንም በአንድም በሌላ ካስተማረን ከኛ ፴(ሠላሳ)፣ ፷(ስልሣ) እና ፻(መቶ) ያማረ ፍሬን ይጠብቃልና የተማርነውን በኑሮ እናትርፍበት! ልክ በቅዳሴ እንደምንታዘዘው ‘አልዕሉ አልባቢክሙ/ልቡናችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ’ ተብለን በምድር ብንኖርም ልቡናችንን ወደላይ ወደ ሰማይ ከፍ አድርገን ከምድራዊ ፍላጎት በላይ በሆነው በእግዚአብሔር ሐሳብ ሕይወታችንን እንምራ።

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ ወለወላዲቱ ድንግል፤ ወለመስቀሉ ክቡር ለዓለም ዓለም አሜን።

መርገመ በለስ

ከመምህር አበበ ፍቅሬ

̎ስንዱ እመቤት” የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሀገራችን ኢትዮጵያ ሀገራዊ የዘመን አቆጣጠር፤ (calendar) ሰርታ ያስረከበች እንደመሆኗ መጠን የእያንዳንዱ የነገረ መለኮት አስተምህሮ፣ ሥርዓተ አምልኮ፤ (Liturgical worship) ፣ አጽዋማት፤ (fasts) ፤ ክብረ በዓላት እኒህን የመሳሰሉ ሁሉ የምታከናውነው ከታላቁ መጸሐፍ ቅዱስ መሠረት አድርጋ በዘመን ቀመር ነው። (ዘፍ. ፩፥፲፬)

ዓመት፣ ወር፣ ሳምንት፣ ቀን፣ ሰዓት እያለ እስከ ሣድሲት መለኪያ በዘመን መስፈሪያ ውስጥ አካታ ቀመራትን ከጥንታት እንደ ̎ድርና ማግ” አሰናኝታ ወቅቶችን በሚገባ አሰናድታ ስትዋጅ እነሆ ሦስት ዐሥር ምእት ዓመታትን ዘልቃለች።

ኢትዮጵያዊው የዜማ ደራሲ ቅዱስ ያሬድ ዐቢይ ጾምን ከአስተምህሮ አንጻር በስምነት ሣመንታት መክፈሉ እሙን ነው። የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት ሥግው ቃል ክርስቶስ ሰው ከመሆኑ በፊት የነበረብንን የሞት ጥላ እንዲሁም የጌታችንን መከራ መስቀል አመጸኛው አዳምን ነፃ ለማውጣት እንደ አመጸኛ ተቆጥሮ የደረሰብን ስቃይ ሁሉ በዓይነ ኅሊናችን ስለን በመከራው ተባብረን በትንሣኤው አንድ እንድንሆን (ሮሜ ፮፥፭) በሚል የዐቢይ ጾም ሳምንታት የመጨረሻዎቹ አምስቱ ቀናት ሰሙነ ሕማማት በሚል ጠርቷቸዋል። የእያንዳንዱ እለታት ከአስተምህሮ ጋር በተያያዘ የራሳቸው ስያሜ ያላቸው ሲሆን፤ የመጀመሪያው የሕማማት እለት ሰኞ ̎መርገመ በለስ፤ የበለስ መረገም” በሚል ተጠርቷል።

ስለበለስ መረገም

̎በማለዳም ወደ ከተማ ሲመለስ ተራበ። በመንገድም አጠገብ በለስ አይቶ ወደ እርስዋ መጣ፤ ከቅጠልም ብቻ በቀር ምንም አላገኘባትምና፦ ለዘላለሙ ፍሬ አይገኝብሽ አላት፤ በለሲቱም ያንጊዜውን ደረቀች።” (ማቴ. ፳፩፥፲፰-፲፱) እንደሚለን ቅዱስ ማቴዎስ አምላካችን በሕጻናቱ አንደበት እንደተመሰገነ ወደቢታንያ አቀንቶ ሰለነበረ ከቢታንያ ሲመለስ ተርቦ ወደበለስ እንደሄደ፣ ፍሬ እንዳላገኘና እንደረገማት ነው የሚያስረዳን።

የአንድምታ ሊቃውንት በትርጓሜ ወንጌል እንዳስቀመጡት በለስ ለሚለው የተለያዩ ትርጉም ሰጥተው ይበይኑታል፤ በዚህም መሠረት

በለስ ቤተ እስራኤል ነው፤ ̎ሕዝበ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ሕዝብ፣ አምላከ እስራኤል፤ የእስራኤል አምላክ” ተብሎ በስሙ የተጠሩት፣ በስማቸው የተሰየመው እንደውም ̎ወልድየ ዘበኲርየ፤ የበኲር ልጄ” ብሎ በቁልምጫ የሚጠራቸው፤ ̎መጽአ ኃበዚአሁ፤ የእርሱ ወደ ሆኑት ወደ ወገኖቹ መጣ።” (ዮሐ. ፩፥፲፩) ብሎ ዮሐንስ በወንጌሉ እንደ ነገረን ወዳጆቹ ተብለው የሚጠሩት ናቸው።

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን በጠላት እጅ ቢወድቁ በዐሥር ታላላቅ ተአምራት ያስለቀቃቸው፣ ፈርዖን እግር ለእግር ቢከታተላቸው በባሕር ያሰጠመላቸው፤ ከአለት ውሀ አፍልቆ ያጠጣቸው፤ ከሰማይ መና አውርዶ የመገባቸው፤ ወደ ከነአን መርቶ ያወጣቸው፤ አሕዛብን አስለቅቆ ከነአንን በመሐላው መሰረት ያወረሳቸው፤ ሲያምጹ እንደልጅ አማሌቃውያንን አስነስቶ የቀጣቸው መልሰው ሲያለቅሱ ደግሞ በወዳጆቹ የታደጋቸው፤ አምላክ ሰው ሆኖ በመካከላቸው ተገልጦ “እውነት እላችኋለሁ፥ ብዙዎች ነቢያትና ጻድቃን የምታዩትን ሊያዩ ተመኝተው አላዩም፥ የምትሰሙትንም ሊሰሙ ተመኝተው አልሰሙም።” (ማቴ. ፲፫፥፲፯) ፤ ̎አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው።” (ዮሐ. ፰፥፶፮) እያለ ቢነግራቸውም ̎ገና አምሳ ዓመት ያልሆነህ አብርሃምን አይተሃልን? አሉት ̎ (ዮሐ. ፰፥፶፯) እንዲያውም “ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ።” (ዮሐ. ፰፥፶፱) እንዲል በሥጋ መገለጡን ሲያዩ ሰውነቱን እንጂ መለከታዊ አካሉን ማየት አልቻሉም፤ ብሉየ መዋእል ጌታን በዕድሜ ገድበውታል። ̎…እነርሱ ግን አልተቀበሉትም።” ዮሐ. ፩፥፲፩) እንዲል ካዱት።

“አብርሃም አባት አለን እንደምትሉ አይምሰላችሁ፤” (ማቴ. ፫፥፱) “መልሰውም፦ አባታችንስ አብርሃም ነው አሉት። ኢየሱስም፦ የአብሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር።” (ዮሐ. ፰፥፴፱) እንዲል ቤተ እስራኤል ስም ብቻ ይዘው የቀሩ ምግባር የጎደላቸው በኢየሱስ ክርስቶስ ከማመን የዘገዩ ነበሩ።

ጌታችን ፍሬ ምግባርና ሀይማኖትን ፈልጎ በመጣ ጊዜ ቅጠል የአብረሀም ዘር መባልን ብቻ ሆነው ቀሩ። በመሆኑም ̎ለዘለዓለም ፍሬ አይገኝብሽ።” ብሎ ረገማት፤ በዚሁ ቃል መሠረት ምንም እንኳ እንደነ ቅዱስ ጳውሎስና እሱን የመሰሉ የወንጌል አርበኞች ቢገኙም ቤተ እስራኤል የብሉይ አማኝ ብቻ ሆና በመቅረት በክርስቶስ ኢየሱስ የሆነው የሐዲስ ኪዳን ሕግን ከመቀበል ገሸሽ ብላለች። እስካሁን የጌታ መምጣቱን ሳትቀበል ገና እንደሚመጣ ስትጠባበቅ በዘመናችን ትገኛለችና፤ ቤተ እስራኤል የሚጠበቅባትን የሀይማኖትና የምግባር ፍሬ ሳይገኝባት በመቅረቷ ተረገመች ወዲያው ደረቀች።

በለስ የተባለች ኦሪት ናት። መተርጕማኑ እንደሚተረጉሙት ኦሪት ̎ፈጻሜ ሕግ፤ የሕግ መፈጸሚያ ከመባል ውጭ ድኅነትን አላደረገባትም። ማለትም ይህንን አድርጉ ይህንን አታድርጉ ብቻ ትእዛዝን ነበር፤ መጽሐፍ ቅዱስ ̎እንኪያስ ሙሴ የፍችዋን ጽሕፈት ሰጥተው እንዲፈቱአት ስለ ምን አዘዘ? አሉት። ሙሴስ ስለ ልባችሁ ጥንካሬ ሚስቶቻችሁን ትፈቱ ዘንድ ፈቀደላችሁ፤ ከጥንት ግን እንዲህ አልነበረም። (ማቴ. ፲፱፥፯-፰) እንደሚለው ሕግን ለመፈጸም የተሰጡ አሉና፤ እንዲሁም መሥዋዕትና ሥርዓተ ክህነቱ ጊዜያዊ ድኅነትን ያሰጡ ዘንድ ፍጹም ድኅነትን ማሰጠት የማይችሉ ሕግጋት ነበሩ። ስለዘህም ሻራቸው፤ ̎እምከመ ተሥዕረት መሥዋዕቶሙ ትሠዐር ክህነቶሙ፤ መሥዋዕታቸው ከተሻረች ክህነታችውም ትሻራለች እንዲል መሥዋዕቱ ከነሙሉ የመሠዊያ ሥርዓቱ ተሻረ፤ ምክንያቱም ዘለዓለማዊ የሆነ የነፍስ ድኅነት በሚያሰጠው በአማናዊ መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ተቀይሯልና ነው።

የክህነት አሰጣጡም ቢሆን ተቀይሯል፤ ቀደም ሲል ክህነት ከሌዊ ወገን ከሆነው ከአሮን ቤት ብቻ ነበር፤ በክህነቱም የሚሠዋው ደመ ነፍስ እንስሳ ሆኖ የሚፈውሰውም ሥጋን ብቻ ነበር፤ የሚታየውም ነቀፋ ነውረ ሥጋ ነበር፤ የሐዲስ ኪዳን ክህነት ግን ሕዝብና አሕዛብ ብሎ በነገድ(ወገን) ሳይለይ በክርቶስ ያመነ ሁሉ የሚሰጥ ክህነቱም የዘለዓለም ኃጢአት ማስተስሪያ ነው፤ መስፈርቱም ነውረ ሥጋ ሳይሆን ነውረ ነፍስ የሆነው ኃጢአት ነው።

ከዚህም ባሻገር ̎ዓይን ቤዛ ዓይን/ ዓይን ያጠፋ ዓይኑ የጥፋ” ተብለው የተሰጡት ዓየነት ሕጎችን “…ከእናንተ ኃጢአት የሌለበት አስቀድሞ በድንጋይ ይውገራት አላቸው።” (ዮሐ. ፰፥፯) “እኔም አልፈርድብሽም፤ ሂጂ ከአሁንም ጀምሮ ደግመሽ ኃጢአት አትሥሪ አላት።” (ዮሐ. ፰፥፲፩) ማንም ስለኃጢአቱ ንሰሐ እንዲገባ እንጂ እንዳይገደል አምላካችን አዟል።

በለስ የተባለው ኃጢአትን ነው። መተርጕማኑ ̎የበለስ ቅጠል ሰፊ እንደሆነ ኀጢአትም በዚህ ዓለም ሰፍና አገኛት።”፤ አንድም በለስ ሲበሉት ይጣፍጣል ቆይቶ ይኮመጥጣል። ኃጢአትም ሲሠሩት ደስ ያሰኛል ኋላ ያሳዝናልና…ፍሬ አይገኝብሽ አላት በአንቺ በመጣ ፍዳ የሚያዝ አይኑር አላት። ኃጢአትም ፈጠና ጠፋች።”

በቀዳማዊ አዳም ምክንያት ሁላችንም ተላላፊዎች ተብለን በኃጢአት ባርነት ሥር ብንሆንም በዳግማዊ አዳም በኢየሱስ ክርስቶስ የተነሳ ሁላችንም ከበደል ከፍደ ነፃ ወጣን፤ በዚህም ማንም በአዳም መተላለፍ የሚጠየቅ እንደሌለና፤ ሁሉም ራሱ ወዶ ፈቅዶ በሚሠራት ኃጢአት የሚጠየቅ መሆኑን አስረዳን።

በባሕርዩ በደል የማይስማማው ንፁሐ ባሕርይ ክርስቶስ ሳይበድል በደለኛ ተብሏል፤ ከወንበዴዎች ጋራ ተሰቅሏል። በእንዲህ ዓይነት ሁኔታ ከባርነት ቀንበርም አላቆናል። መተርጕማኑ እንዳስቀመጡትም ̎ኃጢአት ከሥሩ እንደተነቀለ ዛፍ ሆኗል፤ ከዚህ በኋላ ኃጢአት የሚሰራ ሰው ለተማረከ ወታደር የሚያገለግል ሰው ይመስላል።” 

 ዛሬም አምላካችን ከእያንዳንዳችን ፍሬ ሊፈልግ ይመጣል፤ ገበሬ የተከለው ችግኝ ኮትኵቶ፣ ውሀ አጠጥቶና አርሞ ካሳደገው በኋላ የድካሙን ፍሬ ከዛፉ እንደሚጠብቅ ሁሉ እስከ ሞት ድረስ የሚያደርስ ውድ ዋጋ የከፈለልን አምላካችን ከሁላችንም ፴፣ ፷ና ፻ የሃይማኖት ፍሬ የፈልግብናል

ከዚህ ውጪ ግን ፍሬ የማይገኝብን ከሆነ ̎አሁንም በወይኔ ላይ የማደርገውን እነግራችኋለሁ፤ አጥሩን እነቅላለሁ፥ ለማሰማርያም ይሆናል፤ ቅጥሩንም አፈርሳለሁ፥ ለመራገጫም ይሆናል። ባድማ አደርገዋለሁ፤ አይቈረጥም፥ አይኰተኰትም፤ ኵርንችትና እሾህ ይበቅልበታል፤ ዝናብንም እንዳያዘንቡበት ዳመናዎችን አዝዛለሁ።” (ኢሳ. ፭፥፭-፮) አንዲል ለመከራና ለዋይታ ተላልፈን መሰጠት ይኖራልና፤ ይህ እንዳይሆንብን ከወዲሁ አምላክ በልግስናው በሰጠን ዕድሜያችን ቃሉን ሰምተን እርሱን ደስ የሚያሰኝ ሥራ ልንሰራ ይገባናል። ማለትም

የሀይማኖት፣ የምግባር፣ የፍቅር፣ የአንድነት፣ የመተሳሰብ፣ የመቻቻል ፍሬ ሊፈልግ ይመጣል፤ ለእኛ ብሎ የተቀበላቸውን ጸዋትወ መከራዎችን አስበን እነዚህን ፍሬ አፍርተን ልንጠብቀው ይገባል።

ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይቆየን

ሆሣዕና በአርያም!

ከመምህር ጌራ ሞገስ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ አሜን። በባሕርዩ ሞት በመንግሥቱ ሽረት የሌለበት፤ አንድነቱን ሦስትነቱ የማይከፋፍለው ሦስትነቱን አንድነቱ የማይጠቀልለው ለዘለዓለም አንድ ሲሆን ሦስት ሦስት ሲሆን አንድ እየተባለ የሚመሰገን እግዚአብሔር አምላክ ወዶና ፈቅዶ እንኳንም ለ ፳፻፲፰ ዓ.ም በዓለ ሆሣዕና በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ።

ሆሣዕና

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ከዘለዓለማዊ ሞት የማዳን ሥራውን ለመፈጸም ጥቂት ቀናት ሲቀሩት በነቢያት የተነገረው ትንቢትና በብሉይ ኪዳን የነበረው ምሳሌ ይፈጸም ዘንድ በአህያዪቱና በውርንጫው ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ደቀ መዛሙርቱና ብዛት ያለው ሕዝብ ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› እያሉ በመዘመር ሰማያዊ አዳኝ መሆኑን መስክረው ተቀብለውታል። ሆሣዕና ቃሉ የአረማይክ ሲሆን ትርጉሙም “አሁን አድን” ማለት ነው፡፡

የሆሣዕና በዓል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የትሕትና ንጉሥነት እና የድል ጉዞ የምናስብበት ታላቅ ዕለት ነው። ይህ በዓል በታሪክ ውስጥ የተከናወነ ድርጊት ብቻ ሳይሆን፣ ዛሬ ላለንበት ዘመንና ሕይወት ጥልቅ የሆነ መንፈሳዊ ትርጉም አለው።

ሆሣዕናን እና ያለንበትን ዘመን በሚከተሉት ዋና ዋና ነጥቦች ማየት እንችላለን፦

. ትሕትና እንደ መሪነት መገለጫ

በዓለ ሆሣዕና የዓለምን የሥልጣንና የክብር ትርጉም የለወጠ ዕለት ነው። በወቅቱ የነበሩ ነገሥታት በፈረስና በሰረገላ፣ በጦር መሣሪያ ታጅበው ለጦርነትና ለግርማ ሞገስ ሲወጡ፣ የሰላሙ ንጉሥ ግን በአህያ ውርንጭላ ላይ ሆኖ መጣ።

 “ለጽዮን ልጅ፦ እነሆ፥ ንጉሥሽ የዋህ ሆኖ በአህያ ላይና በአህያይቱ ግልገል በውርንጭላዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል በሏት ተብሎ በነቢይ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሆነ።” እንዲል (ማቴ. ፳፩፥፬-፭) ፤ ዘካ. ፱-፱)

በዘመነ ብሉይ የነቢያቱ ትርኢት ትርጓሜ ወንጌል እንደሚነግረን ዘመኑ ሰላም ሲሆን ነቢይ ወደ ሕዝብ አደባባይ የሚሔደው በአህያ ላይ ተጭኖ ነበር፤ ዘመኑ እስራኤላውያንን እግዚአብሔር ተቆጥቷቸው የጦርነት በር የሚከፈትባቸው እንደሆነ ግን በፈረስ ላይ ተቀምጠው በግልቢያ ነበር የሚከሰቱት፤ የሰላም አለቃ የተባለው ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሥቃይ፣ የመከራ፣ የሰቀቀን ፣ የዋይታ በአጠቃላይ የዲያብሎስ ምርኮ የሆነበት የብሉይ ኪዳን ዘመን አከተመ፤ የሰላም፣ የዕረፍት፣ የሐሴትና የነፃነት ዘመን ተወጠነ ሲል በአህያ ላይ ተቀምጦ መጣ።

ለዘመናችን ትምህርት፦ በዚህ በትዕቢትና በፉክክር በተናወጠ ዓለም ውስጥ፣ እውነተኛ ታላቅነት የሚገኘው በትሕትናና ሌሎችን በማገልገል እንደሆነ ያስገነዝበናል።

. የልብን ምንጣፍ ማንጠፍ (እውነተኛ አምልኮ)

በዓለ ሆሣዕና ሕዝቡ ልብሳቸውንና የዘንባባ ዝንጣፊዎችን በመንገዱ ላይ አነጠፉ። ዛሬ ደግሞ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው የውጭ ልብስን ሳይሆን፣ የልባችንን መከፈትና ንስሓን ነው።

 “ከሕዝቡም እጅግ ብዙዎች ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ፥ ሌሎችም ከዛፍ ዝንጣፊዎችን እየቆረጡ በመንገድ ላይ ያነጥፉ ነበር።” (ማቴ. ፳፩፥፰)

ለዘመናችን ትምህርት፦ ጌታ ወደ ሕይወታችን እንዲገባ የልባችንን ዙፋን ልንሰጠው ይገባል። በይሉኝታና በዘልማድ ብቻ ሳይሆን፣ ውስጣዊ ማንነታችንን ለእርሱ ማስገዛት ይጠበቅብናል።

. “ሆሣዕና” – የድኅነት ጩኸት

“ሆሣዕና” ማለት “አሁን አድን” ማለት እንደመሆኑ፤ በወቅቱ የነበሩ ሕዝቦች ጌታን የተቀበሉት እንደ ፖለቲካ ነፃ አውጪ ቢሆንም፣ እርሱ ግን የመጣው ከኃጢአትና ከዘለዓለም ሞት ሊያድነን ነው።

 “የሚቀድሙትም ሕዝብ የሚከተሉትም፦ ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር።” (ማቴ. 21፡9)

ለዘመናችን ትምህርት፦ ዓለማችን በጦርነት፣ በበሽታና በጭንቀት በታወከችበት በዚህ ዘመን፣ የእኛም ጩኸት “ሆሣዕና – ጌታ ሆይ አሁን አድነን!” ሊሆን ይገባል። እውነተኛ ሰላም ከሰው ሳይሆን ከእግዚአብሔር ብቻ እንደሚገኝ ማመን አለብን።

. የማይለወጥ አቋም (ጽናት)

በሆሣዕና ዕለት “ሆሣዕና” ያሉ ብዙዎች፣ ይሁኑ እንጂ ከጥቂት ቀናት በኋላ ሆሣዕና ብለው ባመሰገኑበት አንደበት “ስቀለው!” በማለት ሲጮኹ ታይተዋል። ይህም የሰው ልጅን ጠባይና የዘመናችንን ክዳት ያሳያል።

ለዘመናችን ትምህርት፦ እምነታችን በሁኔታዎች ላይ የተመሠረተ መሆን የለበትም። ነገሮች ሲመቻቹ የምናመሰግን፣ ሲከፉ ደግሞ የምናማርር መሆን የለብንም። “እስከ መጨረሻው የሚጸና እርሱ ግን ይድናል።” (ማቴ. 24፥13)

ሲጠቃለል ሆሣዕና የሰላም ንጉሥ ወደ ልባችንና ወደ ቤታችን የሚገባበት በዓል ነው። ዛሬም ጌታ በደጃችን ቆሞ ያንኳኳል። እኛም እንደ ኢየሩሳሌም ሕዝብ በደስታ ተቀብለን፣ በሕይወታችን ላይ እንዲነግሥ በመፍቀድ፣ ክርስቶስን መስለን ልንኖር ይገባል።

ወስብሐት ለእግዘአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይቆየን

መልካም የሆሣዕና በዓል!

አገልግሎት

በዲ/ን አብርሃም ባንቲሁን

የሰው ልጅ በፈጣሪው አምሳል ሕያው ባለአእምሮ፤ ነቢብ ሆኖ ሲፈጠር የእግዚአብሔርን ስም ይቀድስ ዘንድ እንዲሁም ዓለም ሳይፈጠር በፊት የተዘጋጀለትን ዘለዓለማዊ ክብር ይወርስ ዘንድ ነው። የእግዚአብሔርን ስም ከሚቀድስባቸው መንገዶች ውስጥ አንዱ ሥጋ እንደ  ለበሰ መልአክ ሆኖ ለአገልግሎት በመትጋት ነው። ‹‹እኛ ፍጥረቱ ነንና እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን በማለት ንዋየ ኅሩይ ቅዱስ ጳውሎስ እንደነገረን›› (ኤፌ. ፪፥፲) ።

አገልግሎት ምንድን ነው?

አገልግሎት በአንድ ቃል ሊወሰን የማይችል ሰፋ ያለ ሐሳብ ነው። አገልግሎት አንድ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ጋር የሚያደርገው ጉዞ ነው። በክርስቶስ ኢየሱስ ያመነውን እምነት፣ በሐዋርያት የተሰበከለትን ወንጌል የሚኖርበት ሕይወት ነው። ክርስትና በቃልና በኑሮ የሚገለጽ ምስክርነት ነው። አገልግሎትም ይህን ሕይወት በመኖር ሌሎች ይኖሩት ዘንድ ብርሃንን መፍጠር ነው። አገልግሎት በሕይወት ላይ ክርስቶስን ንጉሥ አድርጎ መሾም ነው።

በዚህች ምድር ላይ እንኳ ብዙ ዓይነት አገልግሎት ይስተዋላል። ሰው ለባልንጀራው የሚሰጠው አገልግሎት፣ ሰው ለገዢው የሚሰጠው አገልግሎት፣ ሰው ለማኅበረሰቡ የሚሰጠው አገልግሎት አለ። እነዚህ አገልግሎቶች ሥጋዊ አገልግሎቶች ቢሆኑም የኃጢአትን መንገድ እስካልቀላቀሉ ድረስ ሰውን በእግዚአብሔር ዘንድ የሚያስነቅፉ አይደሉም።

እኛ ግን ከነዚህ ሁሉ የሚበልጠውን አገልግሎት እናያለን። ይህም መንፈሳዊ አገልግሎት ነው። መንፈሳዊ አገልገሎት ልዩ ልዩ ነው። ሰው እንደየጸጋው እግዚአብሔርን የሚያከብርበት መንገድ ነው። አገልግሎት ፍቅር ነው፣ አገልግሎት ትሕትና ነው፣ አገልግሎት የንጽሕና ሕይወት ነው፣ አገልግሎት በቅድስና የሚከወን ነው፣ አገልግሎት የሕይወት መንገድ ነው።

አገልግሎት ፍቅር ነው

አገልግሎት ከሰው ልብ የሚፈልቀው ፍቅር የሚገለጽበት መንገድ ነው። ፍቅር እግዚአብሔር ዓለምን ለመፍጠሩ ብሎም በኋለኛው ዘመን ለማዳኑ ምክንያት የሆነ የመንፈስ ፍሬ ነው። ፍቅር የሕግ ሁሉ የበላይ ነው። በፍቅር ውስጥ መታዘዝ እና ርኅራኄ ይሰፍናሉ። ይቅርታ እና ምሕረት ጎልተው ይታያሉ። ፍቅር በልቡ ውስጥ ያለ ሰው እግዚአብሔርን ከፍርዱ ጽናት የተነሣ ሳይሆን ከፍቅሩ ኀያልነት የተነሣ ይፈራዋል።

አገልግሎታችን በእግዚአብሔር የሚያስነቅፈን እንዳይሆን በፍቅር ላይ የተመሠረተ ይሆን ዘንድ ግድ ነው። ለዚህ አብነት ይሆነን ዘንድ ጌታ የኤፌሶንን ቤተ ክርስቲያን የነቀፈበትን ምክንያት ማየት ይበቃል። ‹‹ዳሩ ግን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ የቀደመውን ፍቅርህን ትተሃልና›› (ራዕ.፪፥፬) እግዚአብሔር በአገልግሎታችን ውስጥ ፍቅርን ያይ ዘንድ ይወዳል።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ በተመላለሰበት ዘመን ያደረጋቸው ተአምራት በሙሉ መነሻቸው ፍቅር ነበር። አገልግሎት ለእግዚአብሔር እና ለመንግሥቱ ያለን ፍቅር ነጸብራቅ ነው።

የጥበብ መጨረሻ የተባለው ፍቅር ፍቅረ እግዚአብሔር እና ፍቅረ ቢጽ በመባል ለሁለት ይከፈላል።

ፍቅረ እግዚአብሔር

እግዚአብሔርን መውደድ የአገልግሎት ብቻ ሳይሆን የክርስትና ሕይወትም መሠረት ነው። እግዚአብሔር ለሙሴ ሕግን በሰጠው ጊዜ ከትእዛዛቱ መካከል አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ በፍጹምም ኀይልህ ውደድ የሚለው ዋነኛው ነው። እውነተኛ አገልጋይ እግዚአብሔርን በፍጹም ልቡ በመውደድ ሰዎች እግዚአብሔርን እንዲወዱት የሚያደርግ ነው። ፍቅር የአገልግሎት መለኪያም ጭምር ነው። ለሊቀ ሐዋርያት ለቅዱስ ጴጥሮስ ሦስት ጊዜ የቀረበው የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ ትወደኛለህን? የሚለው ጥያቄ እና የሐዋርያውን መልስ ተከትሎ የተሰጠው የአገልግሎት ኀላፊነት እግዚአብሔር የአገልግሎታችንን መጠን ለእርሱ ባለን ፍቅር ልክ ለመለካቱ ማሳያ ነው።

ፍቅረ ቢጽ

ይህ ዓይነቱ ፍቅር እግዚአብሔር ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ በማለት ያዘዘውን ትእዛዝ የምንፈጽምበት ፍቅር ነው። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህችኛይቱ ፍቅር ‹‹ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና እርሱም፦ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የሚል ነው›› በማለት ይነግረናል። ነገር ግን አንዳንድ ሰዎች ለእግዚአብሔር ያለን ፍቅር በቂ ሊሆን አይችልምን? ለሱ ያለን ፍቅር አገልግሎቱን ለመከወን በቂ ምክንያት አይደለምን? በማለት ሲጠይቁ ይስተዋላሉ፤ ይሁንና የፍቅር ሐዋርያ የተባለ ዮሐንስ እንዲህ በማለት ይመልስላቸዋል ጽድቅን የማያደርግና ወንድሙን የማይወድ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም። ዳግመኛም ሐዋርያው ወንድሙን የሚጠላ ሰው ከነፍሰ ገዳይ የማይለይ እንደሆነ፣ የዘላለም ሕይወት እንደሌለው እና የእግዚአብሔር ፍቅር በልቡ እንደሌለ ያረጋግጥልናል። (፩ኛ ዮሐ.፫፥፲፭-)

አገልግሎት ትሕትና ነው

ትሕትና የክርስቶስ ፍቅርና መሥዋዕትነት ነጸብራቅ ነው። በትሕትና ውስጥ የሕይወትን ትክክለኛ ትርጉም እና ወደ ዘለዓለማዊ ደስታ የሚወስደውን መንገድ እናገኛለን። አገልግሎት የእግዚአብሔር ትሕትና ማሳያ ነው። እርሱ እግዚአብሔር ሁሉን ሥራ በራሱ መከወን የሚችል የሚሳነው የሌለ አምላክ ሆኖ ሳለ ይህን የተቀደሰ አገልግሎት ለእኛ በመፍቀድ የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ተሳታፊ አደረገን። በመዋዕለ ሥጋዌውም ለፍጹም ትሕትና አብነት ሆነን። ‹‹ከእኔም ተማሩ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና››  በማለት ለትሕትና ጠራን።

የታመነ አገልጋይ ልቡ በቅንነት እና በትሕትና የተሞላ ነው፤ ወንድሙ ከእርሱ እንደሚሻል በትሕትና ያስባል። አገልግሎቱም ከንቱ ውዳሴን በመሻት የሚደረግ ሳይሆን የመንፈስ ፍሬዎችን ገንዘብ ያደረገ ይሆናል።

አገልግሎት የንጽሕና ሕይወት ነው

ንጽሕናን የምትሻ ነፍስ በመንፈስ ቅዱስ ለመሞላት የምትጠብቅን ዕቃ ትመስላለች። የእግዚአብሔር አገልጋይ ንጽሐ ልቡና ያለው ነውርና ነቀፋን የሚጸየፍ ነው። አገልግሎት ራስን ለእግዚአብሔር መስጠት ነው። እርሱ የሰጠንን ሀብት ለእርሱ መልሰን መሥዋዕት የምናደርግበት መንገድ ነው። ለእግዚአብሔር የሚቀርብ መሥዋዕት ደግሞ ንጹሕና የተመረጠ ይሆን ዘንድ ይገባል። ራሳችንን ለእግዚአብሔር ስናቀርብ በንጽሕና መሆን አለበት። መሥዋዕታችንም እንደ አቤል መሥዋዕት በአምላክ የተወደደ ይሆናል።

አገልግሎት በቅድስና የሚከወን ነው

እንደ እግዚአብሔር ያለ የቅድስና አስተማሪ ማነው? እንደ አምላካችን ያለ የሚያነጻ ማነው? እርሱ የሰውን ልጅ ለርኩሰት ሳይሆን ለቅድስና ጠርቶታልና። በአገልግሎታችን ሂደትም ይህን የተጠራንበትን ዓላማ ማክበር ይገባናል። ሰውነቱን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርጎ የሰጠ ሰው እግዚአብሔርን በቅድስና ያገለግል ዘንድ ግድ ነውና። አገልግሎት እግዚአብሔርን መስሎ ሌሎች እኛን ይመስሉ ዘንድ መጥራት ነው።  ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ በማለት እርሱን በቅድስናና በንጽሕና ወደመምሰል ይጠራናልና። እኛም እርሱን አብነት በማድረግ ለተቀደሰ አገልግሎት የተዘጋጀን መሆን አለብን።

አገልግሎት የሕይወት መንገድ ነው

አገልግሎት መንገድ ነው፤ ከአንደኛው ሰው ሕይወት ወደ ሌላኛው ሰው ሕይወት እየተሸጋገረ የሚቀጥል መንገድ። የሕይወትን እስትንፋስ ከአንዱ ወደ ሌላው እያዳረሰ የሚቀጥል ጥልቅ ጉዞ። ከሙሴ ወደ ኢያሱ የተሻገረ መንገድ፣ ከኤልያስ ወደ ኤልሳዕ የተሻገረ መንፈስ፣ ከጳውሎስ ወደ ጢሞቴዎስ የተሻገረ ጉዞ። አገልግሎት የሚቀጥል ነው። እግዚአብሔር ለቤቱ አገልጋይን ይተካል። ከትውልዱ መካከልም ብርቱውንና ደገኛውን ያስነሣል።

በእግዚአብሔር ቤት ስናገለግል በትምክህት እና በመታበይ የእግዚአብሔርንም ሕግ በመተላለፍ አይሁን። እግዚአብሔር አገልግሎታችንን ስንንቅ ለሚያከብሩት ይሰጣል። ኤሳው ብኩርናውን ንቆ ሸጠው፣ ያዕቆብ በረከቱን ወሰደ፤ ሳኦል በትዕቢት የእግዚአብሔርን ነቢይ አቃለለ ትእዛዙንም አፈረሰ፣ ዳዊት በትሕትናው ንጉሥ ሆነ፤ ይሁዳ ከክርስቶስ ደቀ መዝሙርነት ይልቅ የገንዘብ ፍቅር በለጠበት ከአገልግሎቱም ተሻረ፣ ስሙም ከሕይወት መዝገብ ተፋቀ፤ ማትያስ በትሕትና የሐዋርያነትን ጉዞ ተቀላቀለ።

ለዚህም አገልግሎታችን በፍቅር፣ በትሕትና፣ በንጽሕናና በቅድስና ያጌጠ፣ ለእግዚአብሔርም የተገባ ይሆን ዘንድ መትጋት አለብን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ኒቆዲሞስ

በዲ/ን ዮርዳኖስ ተክሉ

ኒቆዲሞስ መምህርና የአይሁድ መሪ ሆኖ ሳለ እውነትን ለማወቅ ከክርስቶስ ዘንድ ሊማር በሌሊት መጣ። ራሱን ዝቅ አድርጎ በመማር የትሕትና አርአያ ሆነ። ከዮሴፍ ጋር የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ በሐዲስ መቃብር በጌቴሴማኒ ቀበረ። እኛስ..???

በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ የዐቢይ ጾም የሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዐተ ማኅሌቱ በጾመ ድጓ መጽሐፍ ባዘጋጀው መሠረት የጾሙ ሰባተኛ ሳምንት ኒቆዲሞስ በመባል ይታወቃል።

በዚህ ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት፣ የሚነበበው ወንጌል “ኒቆዲሞስ”ን የሚያወሳ ነው። በዚህ ሰንበት በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት የተጻፈልን፦ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስ ለተባለ የአይሁድ አለቃ ያስተማረው ትምህርት፤ እንዲሁም የኒቆዲሞስ አስተማሪ መምህረ ትሕትና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስን ያስተማረው ትምህርት ይነበባል፣ ይተረጎማል፣ ይዜማል።

          ኒቆዲሞስ ግን ማን ነው?

ኒቆዲሞስ የሚለው ቃል የግሪክ ቃል ሲኾን፤ ትርጉሙም “ድል ማድረግ” ወይም “አሸናፊነት” ማለት ነው። ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ፣ የአይሁድ ሸንጎ አባል የነበረ ከአይሁድ አለቆችና መምህራን አንዱ ነው። (“ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤…” ዮሐ.፫፥፩)

ኒቆዲሞስ መምህር ሲሆን ራሱን ዝቅ አድርጎ የተማረ የትህትና አርአያ ነው። ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ ብቻ ሳይሆን የፈሪሳውያን አለቃ፣ የኦሪት መምህር ብቻ ሳይሆን የኦሪት ምሁርም ነበር። በእርሱ ደረጃ የነበሩ ታላላቅ የአይሁድ ምሁራን መንፈሳዊ ሥልጣናቸውና ሹመታቸው የእግዚአብሔር ስጦታ መሆኑን ረስተው በሕዝቡ ላይ የሚመጻደቁ ነበሩ። በዘመናቸው ዕውቀትን የሚገልጥ እውነተኛ አምላክ፣ የካህናት አለቃ ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም ሲገለጥ የአይሁድ ምሁራን የጌታን መገለጥ አልወደዱትም። የእርሱ ትሕትና የእነርሱን ትዕቢት የሚያጋልጥ ነበርና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚሄዱትን ሁሉ ይነቅፉ ይከስሱ ነበር። ጌታችንም የፈሪሳውያን አሳባቸው በግብዝነት የተሞላና ከንቱም እንደሆነ ነግሯቸዋል። ለደቀ መዛሙርቱም ከጻፎችና ከፈሪሳውያን ጽድቅ የሚበልጥ ሥራን እንዲሠሩ አስጠንቅቋቸዋል። (“እላችኋለሁና፦ ጽድቃችሁ ከጻፎችና ከፈሪሳውያን ጽድቅ ካልበለጠ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት ከቶ አትገቡም።” ማቴ.፭፥፳፤ “ኢየሱስም፦ ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠንቀቁና ተጠበቁ አላቸው።” ማቴ.፲፮፥፮) ኒቆዲሞስ ከእነዚህ ከፈሪሳዊያን መካከል የተገኘ ልዩ ምሁረ ኦሪት ነበር።

የሌሊቱ ደቀ መዝሙር ኒቆዲሞስ

ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊና የአይሁድ ከፍተኛ ሸንጎ አባል ቢሆንም፣ በልቡ ግን እውነትን የማወቅ ከፍተኛ ጥማት ነበረው። ኒቆዲሞስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያደርጋቸውን ተአምራት ሲያይ፣ እሱ ከእግዚአብሔር ዘንድ የመጣ መሆኑን አመነ። ነገር ግን የአይሁድ መሪዎችን በመፍራት በግልጽ ሊከተለው አልደፈረም። ስለዚህ በሌሊት ወደ ጌታ መጣ።

ኒቆዲሞስ ራሱን ለእውነት፣ ልቡን ለእምነት አዘጋጅቶ ከዅሉ ቀድሞ በሌሊት ክርስቶስን ፍለጋ የመጣ ከእነዚህ ፈሪሳዊያን ወገን ተለይቶ እንደ አባታችን አብርሃም ወደ ጽድቅ መንገድ የተጠራ ነው። ኒቆዲሞስ ሹመት እያለው፤ ዕውቀት እያለው፤ ሀብት እያለው ሁሉ ሳይጎድልበት እውነትን ለማወቅ እልቅናው ሳይታሰበው ከአካባቢው ጋር መመሳሰልን ሳይመርጥ ራሱን ዝቅ አድርጎ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሊማር በሌሊት መጣ። መምህረ ትሕትና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የኒቆዲሞስን ትሕትናውን ተቀብሎ “ለምን በቀን አትመጣም?” ሳይለው እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ትውልድ ሁሉ የሚማርበትን ረቂቁን ምሥጢር “ምሥጢረ ጥምቀት”ን አስተማረው፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም” (ዮሐ.፫፥፫) አለው። ኒቆዲሞስ መጀመሪያ ነገሩ ግራ ገብቶት “ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?” (ዮሐ.፫፥፬) ብሎ ጠይቆ ነበር። ጌታም ልደቱ ከሥጋ ሳይሆን “ከውኃና ከመንፈስ” (በጥምቀት) መሆኑን አስረዳው፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም” (ዮሐ.፫፥፭)።

ለምን ይሆን ኒቆዲሞስ ከቀኑ ክፍለ ጊዜ ይልቅ የሌሊቱን ጊዜ ለትምህርት የመረጠው ?

ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነው ኒቆዲሞስ ቀን ቀን በአይሁድ ወንበር በሸንጎ እየዋለ ሌሊት ሌሊት ደግሞ ጌታችን ዘንድ እየመጣ ቃለ ወንጌልን ይማር ነበር። ከጌታችን ዘንድ ለመማር ሌሊቱን የመረጠበትም ምክንያት እነሆ፦

፩- የአይሁድ መምህር ስለነበር ስማር ብዙ ሰዎች ሲያዩኝ በውዳሴ ከንቱ መምህር መባል ይቀርብኛል ብሎ፤ እንዳያዩት ፈርቶ ሌሊት እየመጣ ይማር ነበር።

፪- ከቀን ልብ ይልቅ የሌሊት ልብ የተካተተ ስለሆነ በሙሉ ልቡ በማስተዋል ለመማር ስለፈለገ ከቀኑ ክፍለ ጊዜ ይልቅ የማታውን መረጠ።

፫- ሌሊት ጨለማ ነው፤ ብርሃን የለም ጨለማ የኃጢአት ምሳሌ ነው። ኒቆዲሞስ በሌሊት መምጣቱ በኃጢአት እንዳለ ንስሐ እንደሚፈልግ የሚያስረዳን ነው።

፬- ሌሊት የብሉይ ኪዳን ምሳሌ ነው። ኒቆዲሞስም “እኔ ምሁረ ኦሪት እንጂ ምሁረ ወንጌል አይደለሁም። ወንጌልን ካንተ እማር ዘንድ ያስፈልገኛል” ሲል በሌሊት ይመጣ ነበር።

ኒቆዲሞስ ከጨለማ ተማሪነት ወደ ብርሃን ምስክርነት

የኒቆዲሞስ ታሪክ አንድ ሰው ከጥርጣሬና ከፍርሃት ወጥቶ እንዴት የክርስቶስ እውነተኛ ምስክር ሊሆን እንደሚችል የሚያሳይ ትልቅ ትምህርት ነው።

ኒቆዲሞስ በልቡ ያደረው የጌታ ፍቅር እያደገ ሲመጣ፤ አይሁድ ጌታን ያለ ጥፋቱ ሊይዙትና ሊፈርዱበት በሚያሴሩበት ጊዜ፣ በሸንጎው መካከል በድፍረት ቆሞ፦ “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” (ዮሐ.፯፥፶፩) በማለት ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሟገተ። ይህ የሚያሳየው ኒቆዲሞስ ቀስ በቀስ ከፍርሃት እየወጣና ለጽድቅ/ለእውነት መቆም እየጀመረ እንደነበር ነው።

የዕለተ ዓርቡ ታላቅ ምስክርነት

የኒቆዲሞስ እውነተኛ ፍቅርና ድፍረት በጉልህ የታየው ጌታችን በተሰቀለበት ዕለት በዕለተ ዓርብ ነው። ደቀ መዛሙርቱ በፈሩበትና በሸሹበት በዚያ አስጨናቂ ሰዓት፣ ኒቆዲሞስ ግን ፍርሃቱን አስወግዶ ማንነቱን በግልጽ አሳወቀ።

ኒቆዲሞስ ከጌታችን በተማረው ትምህርት ጸንቶ ለመኖር የበቃ ታላቅ አባት ነው። የሃይማኖቱ ጽናትም በተግባር የተፈተነ ነው። ለዚህም ማሳያ የሚሆነን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለ ጊዜ የአርማትያስ ሰው ከሚሆን ከዮሴፍ ጋር በመሆን የአይሁድን ድንፋታ ሳይፈራ “እሱን ያገኘ ያገኘኛል” ሳይል በድፍረት የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውን ከጲላጦስ ለምኖ፤ መቶ ንጥር የሚያህል የከርቤና የእሬት ቅልቅል ይዞ መጥቶ (በወቅቱ ይህ በጣም ውድና ለነገሥታት ክብር የሚቀርብ ሽቶ ነበር)፤ ከዮሴፍ ጋር የጌታን ቅዱስ ሥጋ በንጹሕ የተልባ እግር በፍታ ከሽቶ ጋር ገነዙት፤ በጌቴሴማኒም በአዲስ መቃብር ቀበሩት።

የጌታችንን ክቡር ሥጋ ገንዘው ሲቀብሩም በጸናች የተዋሕዶ እምነት ጌታችን እንደገለጠላቸው “ቅዱስ እግዚአብሔር፣ ቅዱስ ኃያል፣ ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት…” የሚለውን ጸሎት እስከ ፍጻሜው እየጸለዩ ነበር። በዚህም ኒቆዲሞስ ከሐዲስ ኪዳን ካህናት ቀድሞ ምሥጢረ ጥምቀትን ከጌታ እንደተማረ፣ የሐዲስ ኪዳንን የምሥጢራት አክሊል ምሥጢረ ቁርባንንም እንዲሁ ተማረ። ይህንንም በሚመለከት ሊቁ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ አብሮት ይቀድስ የነበረውን ንፍቅ ካህን በባረከበት አንቀጽ “በዚህ ምሥጢር እየተራዳኝ ከእኔ ጋር ያለ ይህንን ካህን እርሱንም እኔንም ሥጋህን እንደገነዙት እንደ ዮሴፍና እንደ ኒቆዲሞስ አድርገን” እንዲል (ቅዳሴ ማርያም ቁጥር ፻፲፭/115)።

በሌሊት ተደብቆ የመጣው ኒቆዲሞስ፣ በመጨረሻ በፀሐይ ብርሃን ለዓለም ሁሉ በሚታይ ሁኔታ የጌታ አገልጋይ መሆኑን በተግባር አረጋገጠ።

እኛስ ዛሬ እንደ ኒቆዲሞስ እውነተኛ የክርስቶስ ወዳጆች ለመሆን ምን ያስፈልገናል?

‎ከኒቆዲሞስ ታሪክ የምንማራቸው ሰባት(፯) ዋና ዋና ነጥቦች፦

፩- ፍርሃትን ማሸነፍ (ከሌሊት ወደ ብርሃን መውጣት)

ኒቆዲሞስ መጀመሪያ አካባቢ “ሰው ምን ይለኛል?” ብሎ በመፍራት በሌሊት ነበር የመጣው። እኛስ ዛሬ በጓደኞቻችን ወይም በቤተሰባችን ዘንድ ላለመናቅ ብለን የምንደብቀው በጎ ማንነት ወይም እምነት አለን?

ስለአንዲቱ ሃይማኖታችን ቆመን ለመመስከር መጀመሪያ በውስጣችን ያለውን የሰው ፍርሃት በእግዚአብሔር ፍቅር መተካት ያስፈልገናል (ከጨለማ ወደ ብርሃን እንውጣ)።

፪- ትኅትና፦ ኒቆዲሞስ ትልቅ ምሁርና መሪ ቢሆንም፣ ያላወቀውን ነገር ለመማር በጌታ እግር ሥር ተደፍቷል። እርሱ መምህር ቢሆንም ጣት ከጣት እንደሚበልጥ ከመምህር መምህር ይበልጣና ለመማር በትኅትና ወደ ክርስቶስ ሄደ በዚያች ትሕትናውም መምህር ፍለጋ ሄዶ አምላኩን አገኘ፤ የሕይወትንም ቃል ሰማ። ስለዚህ እኛም እንደኒቆዲሞስ የሕይወትን ቃል እንሰማ ዘንድ ትኅትናን ገንዘብ ልናደርግ ይገባናል።

፫- የማወቅ ፍላጎት (ለትምህርት ጊዜ መስጠት)

ኒቆዲሞስ ምንም እንኳን የቀኑ ክፍለ ጊዜ ባይመቸውም በሌሊቱ ሰዓት ለመማር ችሏል፤ እኛም  ከእሱ ተምረን “ከልብ ካለቀሱ ዕንባ አይገድም” እንዲሉ ምንም ሥራ ቢበዛብን ቅዱስ ቃሉን የምንማርበት ጊዜ አይጠፋምና ሕይወት ለሚገኝበት ትምህርት ጊዜ ልንሰጥ ይገባናል።

፬- እድገት/ለውጥ፦ ኒቆዲሞስ በእምነቱ እያደገ እንደሄደ ማለትም ከሌሊት/ ከፍርሃት ተነሥቶ እስከ ቀራንዮ አደባባይ/መስቀል ሥር እንደደረሰ፤ እኛም በእምነታችን ጠንክረን ባለንበት ቦታና ሁኔታ ሁሉ ያለፍርሃት እስከሞት ድረስ ስለአንዲቱ ሃይማኖታችን ልንመሰክር ይገባናል።

፭- እውነትን በድፍረት መናገር (በሸንጎው ፊት መቆም)

ኒቆዲሞስ አይሁድ ጌታን ያለ ጥፋቱ ሲከሱት “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” (ዮሐ.፯፥፶፩) ብሎ ተከራክሯል። እኛስ ጓደኞቻችን አንድን ሰው ያለአግባብ ሲያሙ ወይም ሲሳለቁ አይተን “ይህ ስህተት ነው” ብለን የመገሰጽ ድፍረት አለን?

እውነተኛ ክርስቲያን ማለት አብዛኛው ሰው ስህተት በሆነ መንገድ ሲጓዝ፣ እርሱ ብቻውን ቢሆንም እንኳ በእውነት መንገድ ላይ በመጽናት የሚጓዝ ነው።

፮- መሥዋዕትነት (ምርጥ ስጦታን መስጠት)፦ ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር በንግግር ብቻ ሳይሆን በዕለተ ዓርብ እንደታየው በሕይወታችን፤ በጊዜያችንና በንብረታችን መስዋዕትነት ከፍለን መግለጽ ይገባናል። ኒቆዲሞስ ለጌታ ቀብር እጅግ ውድ የሆነ ሽቶ ይዞ መጥቷል። እኛ ለፈጣሪያችንና ለሰዎች የምንሰጠው “ውድ” የምንለው ነገር ምንድን ነው? ወይስ የተረፈንን ብቻ ነው የምንሰጠው?

እውነተኛ ሃይማኖት ከመሰጠትና ከመስጠት ጋር የተያያዘ ነው። ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን እስከሞት ድረስ አሳልፎ በመስጠት እንደወደደን፤ እኛም በፍጹም ፍቅር ራሳችንን አሳልፈን ልንሰጠው ይገባናል። ለሰዎች/ለባልንጀሮቻችን ደግሞ እንደራሳችን አድርገን ወድደናቸው፤ ለእኛ የሚያስፈልገን ሁሉ ለእነርሱም ያስፈልጋቸዋልና ካለን ላይ ልንሰጣቸው ይገናባል።

፯- በመከራ ጊዜ አለመሸሽ (በመስቀሉ ሥር መገኘት)

ብዙዎች ጌታን ጥለውት በሸሹበት ሰዓት ኒቆዲሞስ ግን በግልጽ ወጥቶ ሥጋውን ተቀብሏል። እኛስ ነገሮች ሲበላሹና መከራ ሲመጣ በጽናት እንቆማለን ወይስ እንደ ደቀመዛሙርቱ እንሸሻለን?

እውነተኛ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን የሚታወቀው በደስታ ጊዜ ብቻ ሳይሆን በፈተና ወቅት በሚያሳየው ታማኝነት፤ በመከራ ጊዜ ስለሃይማኖቱ በሚያደርገው ተጋድሎ (ሰማዕትነት)ነው።

‎‎ኒቆዲሞስ ጉዞውን በጥያቄ ጀምሮ በእምነትና በተግባር ጨረሰ። እኛም ዛሬ የክርስትና ሕይወታችን ከቃላት አልፎ በተግባር የተገለጠ እንዲሆን እነዚህን የኒቆዲሞስን ጠንካራ ጎኖች ልንላበስ ይገባል። ለዚህም አምላከ ኒቆዲሞስ ብርታቱንና ጽናቱን ያድለን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር