በዓለ ክብሩ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ ሠለስቱ ደቂቅን (አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል) ከነደደ እሳት ያዳነበትን መታሰቢያ በዓል በድምቀት ታከብራለች፡፡

ቅዱስ ገብርኤል አብሣሪ መልአክ እንደሆነ ሁሉ ምእመናን እግዚአብሔርን በማምለካቸው ምክንያት ከአላውያን ገዢዎች ከሚደርስባቸው መከራም የሚታደጋቸው መልአክ ነው፡፡ የፋርስ ንጉሥ የነበረው ናብከደነፆር እግዚአብሔር አምላክ ምድሪቱን እና ሕዝቡን ያስተዳድር ዘንድ ቢፈቅድለት በትዕቢት ተሞልቶ “በኃይሌ አደርጋለሁ፣ በማስተዋል ጥበቤም የአሕዛብን ድንበሮች አርቃለሁ፣ ሀብታቸውንም እዘርፋለሁ፣ የሚቀመጡባቸውንም ከተሞች አናውጣለሁ፣ በእጄም ዓለምን ሁሉ እንደ ወፍ ቤት እሰበስባለሁ፣ እንደ ተተወ እንቁላልም እወስዳቸዋለሁ፤ ከእኔም የሚያመልጥ የለም፤ የሚቃወመኝም የለም” ብሎ በመታበይ የወርቅ ጣዖትን አሠርቶ በባቢሎን አውራጃ ቁመቱ ስድሳ ክንድ፣ ወርዱም ስድስት ክንድ የሆነ የወርቅ ምስል አሠርቶ በዱራ ሜዳ ላይ አቆመው፡፡ (ኢሳ. ፲፥፲፫-፲፬፤ ዳን.፫፥፩)፡፡

መኳንንትንና ሹሞቹን እንዲሁም ሕዝቡን አስጠርቶ በዐዋጅ ነጋሪ “ንጉሡ ናቡከደነፆር ላቆመው ለወርቁ ምስል ስገዱ፤ ወድቆም የማይሰግድ በዚያን ጊዜ በሚነድ እሳት እቶን ውስጥ ይጣላል” ሲል ዐዋጅ አስነገረ፡፡ ይህን ዐዋጅ የሰሙ የንጉሥ ሹማምንት ሁሉ ተደፍተው ለወርቁ ምስል ሰገዱ፡፡ ነገር ግን በመካከላቸው አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል ንጉሡ ላቆመው ምስል አልሰገዱም፡፡

ነገር ሠሪዎችም ይህንን ወሬ ለንጉሥ ባደረሱ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ ካስጠራቸው በኋላ “… አምላኬን አለማምለካችሁ ላቆምሁትም ለወርቁ ምስል አለመስገዳችሁ እውነት ነውን?” ሲል ጠየቃቸው፡፡

አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል ግን በንጉሡ ፊት ቆመው “ንጉሥ ሆይ፥ እኛ የምናመልከው አምላክ በሰማይ አለ፡፡ ከሚነድደው ከእቶኑ እሳት ያድነን ዘንድ ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል፡፡ ንጉሥ ሆይ! ይህም ባይሆን አማልእክትህን እንዳናመልክ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንዳንሰግድ ዕወቅ” አሉት፡፡ (ዳን.፫፥፬፫-፲፰)፡፡

የንጉሥ ናቡከደነፆር ቁጣ ከፊት ይልቅ እጅግ ነደደ፤ እሳቱንም ሰባት እጥፍ እንዲያቀጣጥሉና እነዚህን ሦስት ብላቴኖች እጅና እግራቸውን አስረው ከእቶን እሳት ውስጥ እንዲጨምሩአቸው አዘዘ፤ ጋሻ ጃግሬዎቹም ፈጥነው ወደሚነደው እሳት ጨመሯቸው፡፡ እግዚአብሔርም የሦስቱን ወጣቶች የእምነት ጽናት ተመለከተ፡፡ በፊቱ የሚቆመውን ባለሟሉን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤልንም ከመጣባቸው መከራ ይታደጋቸው ዘንድ ላከላቸው፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ከእስራታቸው ፈታቸው፤ እሳቱንም እንደ ውኃ አቀዘቀዘው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅም ከተጣሉበት ሆነው መልአኩን ልኮ ከዚህ እቶን እሳት ያዳናቸውን አምላክ አመሰገኑት፡፡

ንጉሡ ናብከደነፆርም ሠለስቱ ደቂቅ እሳቱ አንዳች ጉዳት ሳያደርስባቸው በእሳት ውስጥ ሲመላለሱ ተመለከተ፡፡ “እነሆ እኔ የተፈቱ በእሳቱም መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎችን በዚያ አያለሁ ምንም የነካቸው የለም፤ የአራተኛውም መልክ የእግዚአብሔርን ልጅ ይመስላል” ብሎ ፊቱን ጸፍቶ አፉንም ከፍቶ እንዲናገር አደረገው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅ በእሳቱ ውስጥ ሆነው እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ሰማቸው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ከነደደው እሳት አዳናቸው፡፡ (ዳን. ፫፥፳፬-፳፮)

ናብከደነፆር የተደረገውን ተአምር ተመልክቶ ወደ እሳቱ በመቅረብ ለሦስቱ ብላቴኖች  “እናንተ የልዑል አምላክ ባሪያዎች ሲድራቅ፣ ሚሳቅንና አብደናጎም ኑ ውጡ” ብሎ ተናገራቸው፡፡ (ዳን.፫፥፳፮) እነርሱም እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ወጡ፡፡ መሳፍንቱና ሹማምቶችም የሚያመልኩት አምላካቸው ቅዱስ እግዚአብሔር የሚነደው እሳት ሰውነታቸውን ሳይበላ፣ የራሳቸውም ጸጉር ሳይነካ፣ የእሳቱም ሽታ በላያቸው እንዳልነበረ አዩ፡፡ ንጉሡ ናቡከደነፆርም በሠለስቱ ደቅቅ ፊት ለእግዚአብሔር ሰገደ፡፡ እግዚአብሔርንም እያመሰገነ ሕዝቡን ሁሉ የብላቴኖቹ ሠለስቱ ደቂቅን አምላክ እንዲያመልኩ፤ አናመልክም በሚሉትና የስደብን ነገር በሚናገሩት ላይ ከፍተኛ ቅጣት እንደሚደርስባቸው ዐዋጅ አስነገረ፡፡ ሚሳቅን፣ ሲድራቅና አብደናጎምንም በባቢሎን አውራጃ ውስጥ ሾማቸው፡፡ ከፍ ከፍም አደረጋቸው፡፡

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ልጆቿን ከእነዚህ ብላቴኖች የእምነት ፍሬ ተምረው፣ የመልአኩ ቅዱስ ገብርኤልንም ተራዳኢነት ተረድተው እግዚአብሔርን በማምለክ እንዲጸኑ ታኅሣሥ ፲፱ ቀንን ትዘክራለች፤ በታላቅ ድምቀትም ታከብረዋለች፡፡

የመላእክት አለቃ የቅዱስ ገብርኤል ምልጃና ተራዳኢነት አይለየን፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

በዓታ ለማርያም

ንጽሕተ ንጹሐን፣ ቅድስተ ቅዱሳን፣ ከተመረጡ የተመረጠች፣ ከተለዩ የተለየች፣ ከተከበሩ የተከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእናቷ ከቅድስት ሐናና ከአባቷ ቅዱስ ኢያቄም በእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃድ ከተወለደችበት ዕለት ግንቦት ቀን ጀምሮ በወላጆቿ ቤት ለሦስት ዓመት ከኖረች በኋላ ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ታኅሣሥ ቀን “በዓታ ለማርያም” በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡

ኢያቄምና ሐና የተሳሉትን ስእለታቸው አስታውሰው ወስደው ለቤተ እግዚአብሔር ሲሰጧትም ካህኑ ዘካርያስ ስለምግቧ ተጨነቀ፤ ሕዝቡንም ሰብስቦ ሳለ መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፤ ዘካርያስ ለእርሱ የመጣ ሀብት መስሎት ታጥቆ እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ ከስምዖን ጀምሮ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም በተራ ቢሞክሩ በተመሳሳይ መልኩ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ “ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ” ብለው ሐና እና ኢያቄም እንዲቀርቡ አደረጓቸው፤ ነገር ግን ለእነርሱም ራቀባቸው፤ ዘካርያስም ሐናን “እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ›” አላት፤ በዚያም ጊዜ ቅድስት ማርያም እናቷን ስትከተል መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መገባት፤ ከዚያም በክብር ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱና ሕዝቡም “የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር” ብለው ወደ ቤተ መቅደስ አስገቧት፡፡

ለ፲፪ ዓመታትም ቅድስት ድንግል ማርያም ሰማያዊ ኅብስትና መጠጥ እየተመገበች በቤተ መቅደስ ኖረች፡፡ በ፲፭ ዓመቷ ግን ለአቅመ ሔዋን በመድረሷ ከቤተ መቅደስ ትውጣልን በማለት አይሁድ በጠላትነት ተነሡባት፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ይህን ሰምቶ እመቤታችንን እንዲህ ብሎ ጠየቃት፤ “ኦ ወለተ እስራኤል እፎ ትፈቅዲ ትንበሪ፤ ልጄ እንደምን ሆነሽ ልትኖሪ ትወጂያለሽ?” እርሷም “ከእግዚአብሐር በታች ያለኸኝ አባት አንተ ነህ፤ በዚያውም ላይ እናት አባቴ አደራ ያሉህ አንተን ነው፤ ወደ እግዚአብሔር አመልክትልኝ” አለችው፡፡ ካህኑ ዘካርያስም በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ እንዲህ ብሎ አዘዘው፤ “ከነገደ ይሁዳ ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን በትራቸውን ሰብስበህ በቀዳማይ ሰዓተ ሌሊት ከቤተ መቅደስ አግብተህ ስትጸልይ እደር፤ በቀዳማይ ሰዓተ መዓልት አውጣው፤ ምልክትም አሳይህአለው፡፡” እርሱም እንዳለው አድርጎ በማግሥቱ በትሮቹን አውጥተው ቢያዩ የአረጋዊው ዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩ ጫፍ ላይ “ኦ ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ፥ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት” የሚል ጽሑፍ አገኙ፤ ርግብም መጥታ በራሱ ላይ ዐረፈች፤ ስለሆነም ዮሴፍ እንዲጠብቃት ተወሰነ፡፡

ከዚህም በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከቤተ መቅደስ ወጥታ እስከተሰደደችበት ወራት ድረስ ዮሴፍ ቤት ኖረች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልመኗ ክብሯ በሁላችን ላይ ይደርብን፤ አሜን፡፡

“ታገኙ ዘንድ ሩጡ” (፩ኛቆሮ. ፱፥፳፬)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በግሪክ ከነበሩ አውራጃዎች አንዷ ከሆነችው አካይያ መዲና ቆሮንቶስ ከተማ ገብቶ ለሕዝቡ ጌታ ከፅንሰቱ ጀምሮ ያደረገውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ ቢነግራቸው ብዙዎቹ ከጣዖት አምልኮ እግዚአብሔርን ወደ ማምለክ፣ ኃጢአትን ከመሥራት ጽድቅን ወደ ማድረግ ተመለሰው፤ አምነው ተጠመቁ፡፡ (ሐዋ. ፲፰፥፩–፲)

ቅዱስ ጳውሎስ የቆሮንቶስ ከተማን ሕዝብ አስተምሮ፣ አሳምኖና አጥምቆ ካቆረባቸው በኋላ ከዚያ ወጥቶ ወደ ኤፌሶን ሄደ፡፡ ነገር ግን በቆሮንቶስ ያሉ ምእመናን አስተምሮ ዋጋ ይቀበላል (ገንዘብ ይቀበላል) ብለው አሙት፡፡ ይህንን ሐሜታቸውን ሰምቶ ተስፋ ሳይቆርጥ የወንጌል አገልግሎቱን፣ ማለትም መንፈሳዊውን ትምህርት በሰፊው ቀጥሎበት ለቁመተ ሥጋ ያህል በምእመናን ገንዘብ መመገብ ምንም ቁም ነገር እንዳልሆነ፣ ምንም ሥጋዊ ጥቅም እንደማይፈልግና ገንዘብም እንዳልተቀበላቸው በትምህርቱ ውስጥ ይገልጥ ነበር፡፡ ይልቁንም ቅዱስ ጳውሎስ ይተጋ የነበረው ወንጌልን ስለማስተማር፣ ሰዎችንም ለድኅነት ለማብቃት እንደ ሕጋቸው፣ እንደ አኗኗራቸው ሁሉ እየኖረ ወንጌልን በመስበክ በዓለም በሚደረግ ሰልፍ፣ ሩጫና ሽልማት እየመሰለ ከክርስትና የሚገኘውን ክብር አስተምሯቸዋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በእሽቅድምድም ሥፍራ የሚሽቀዳደሙ ሁሉ እንደሚፋጠኑ አታውቁምን? ለቀደመው የሚደረግለት ዋጋ አለ፤ እንዲሁ እናንተም እንድታገኙ ፈጽማችሁ ሩጡ ይላል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፱፥፳፬) በጦር ሜዳ ተሰልፎ እየፎከረ፣ ጠላቱን ድል የሚያደርግ አርበኛ (ጦረኛ) ከጌታው ዘንድ ሹመት፣ ሽልማት እንዲያገኝ እንዲሁ መንፈሳዊ አርበኛ የሚሆኑ ምእመናንም በምግባር በትሩፋት እየተሸቀዳደሙ ዋጋቸውን (ክብራቸውን) ያገኙ ዘንድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አጥብቆ ይመክራቸዋል፡፡

መሮጥና ማግኘት የሚሉትን ፀንሰ ሐሳቦች ሐሳብ በሁለት መንገድ ማየት እንችላለን፡፡ አንደኛው፡- በዚህ ዓለም በሚደረግ የሩጫ ውድድር አንጻር በክርስትና የሚደረግ የሕይወት ዕድገትና መንፈሳዊ ፉክርክር ነው፡፡ አትሌቶች ሀገራቸውን ወክለው በሩጫ ተወዳድረው አሸናፊ ሆነው ተሸልመው የራሳቸውንም የሀገራቸውንም ስም በዓለም ያስጠራሉ፤ ሥጋውያን ሯጮችም ሲሮጡ በመንገዳቸው ላይ የሚደርስባቸውን ድካም የሚገጥማቸውንም መሰናክል ተቋቁመው የሚያልፉትና ለአሸናፊነት የሚበቁት በአሸናፊነታቸው የሚያገኙትን ክብርና ሽልማት ተስፋ በማድረግ ነው፡፡ ይህንንም ተስፋ ሳይጠራጠሩ እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት ይሮጣሉ፡፡

መንፈሳውያን ሯጮች የሆኑ ምእመናንም እንዲሁ በኅሊናቸው ከዚህ ዓለም ድካምና ፃዕር በኋላ ያለውን የዘለዓለም ሕይወትና የማያልፍ ተድላ ደስታን እያሰቡ ወደ መንግሥተ ሰማያት በእግረ ኃሊናቸው በጽናት ይሮጣሉ፡፡ በሕይወት መንገዳቸው ላይ ከፈቃደ ሥጋቸው፣ ከአጋንንትና ከዐላውያን ነገሥታት ሁሉ የሚደርስባቸውን የቅድስና ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ሩጫ መሰናክሎችን በፍጹም እምነትና በጽናት አሸንፈው በእግዚአብሔር ዘንድ የዘለዓለማዊው ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ተሸላሚ ይሆናሉ፡፡

ክርስቲያን ሁል ጊዜም በምግባረ ክርስትና የሚሮጥ (የሚያድግ) ነው፤ ምግባረ ክርስትና እግዚአብሔርን የምንመስልበት ሕይወት ነው፡፡ ሐዋርያው እኔ ክርስቶስን እንድመስለው እናንተም እኔን ምሰሉ እንዳለ፡፡ (፪ኛቆሮ. ፲፩፥፩) በጥንተ ፍጥረትም አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር ሰውን በአርአያችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠር” ብሎ እርሱን የመምሰል ሕይወት በሰው እንደሚገለጥ ተናግሯል፡፡ (ዘፍ. ፩፥፳፮) እግዚአብሔር ደግሞ በባሕርዩ መልካም ነው፤ ለመልካምነቱም ገደብ የለውም፡፡

ምግባረ ክርስትና ገደብ የለውም፤ ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡ እስከ አሁን የጾምኩት፣ የጸለይሁት፣ ያስቀደስኩት፣ የቈረብኩት ይበቃኛል፣ … አይባልም፡፡ ምክንያቱም የምንነሣበት እንጂ የምንደረስበት ምግባር የለምና፣ በጎነት መጨረሻ የለውም፡፡ ስለዚህ የክርስቲያን ኑሮው ሁል ጊዜ በሩጫ (በበጎ ምግባር መገሥገሥ) ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እጄን እዘረጋለሁ ያለውም ለዚህ ነው፡፡ (ፊል. ፫፥፲፫) ተክል እንደተተከለ ብቻ ከቀረ ይደርቃል እንጂ አያድግም፡፡ ስለዚህ አድጎ ፍሬ እንዲያፈራ ይኮተኮታል፤ ከአፈር፣ ከአየር እና ከውኃ ይመገባል፡፡  ከዚህም የተነሣ አድጎ፣ ለምልሞና አብቦ ያፈራል፤ ክርስቲያናዊ ሰውም እንዲሁ ነው፡፡ በሃይማኖትና በጥምቀት፣ ይተከላል፤ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይመገባል፤ በምግባር ለምልሞ፣ በትሩፋት አብቦ የክብር ፍሬ ያፈራል፡፡ ስለዚህ በክርስትና ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡

በክርስትና ሕይወት ውስጥ ምግባር ሃይማኖት እዚህ ጋር ይበቃኛል ብለን የምናቆመው ሳይሆን ዕለት ዕለት መሽቀዳደም፣ ለፍቅር፣ ለየዋሀት፣ ለቅንነት፣ ለለጋሥነት፣ ለርኅራኄ … መፎካከር ነው፡፡ ሐዋርያው ፍቅርን ተከተሏት” በማለት እንዳስተማረን፡፡ (፩ኛቆሮ. ፲፬፥፩) እንዲህ ከሆነ በሰማይ የሚገኘው ክብር ታላቅ ነው፡፡ ክብር ሁሉ በሥራ መጠን ነውና ለሁሉም እንደ ዋጋው እከፍለዋለሁ እንዳለው አምላካችን ጥቂት የሠራ ጥቂት ክብር ይቀበላል፤ አብዝቶ የሠራም አብዝቶ ይቀበላልና፡፡ (ራእ. ፳፪፥፲፪)

ሁለተኛው በጦር ሰልፍ በሚደረግ ሩጫ አንጻር በተጋድሎ የሚገኝ ጸጋን ለማመልከት ነው፡፡ ከላይ እንዳየነው የጦር ሰልፍ ሩጫ ጠላትን ድል አድርጎ ነፃነትን ማወጅ፣ ከድል በኋላ የሚገኝን ሹመትንና ሽልማትን ገንዘብ ማድረግ፣ ክብርንና አዎንታዊ የታሪክ ባለቤት መሆንን መቀዳጀት ነው፡፡ ስለዚህ ሥጋውያን ጦረኞች እግራቸውን ለጠጠር፣ ግንባራቸውን ለጦር ሰጥተው ከድል በኋላ ስለሚያገኙት ሽልማት እኔ ልዝመት እኔ ልዝመት ብለው ይሽቀዳደማሉ፡፡

ከተጋድሎ በኋላ የሚያገኘውን ክብር የሚያስብ ክርስቲያንም እንደዚሁ ዲያብሎስ ያሰለፈውን ጦር ድል ለመንሣት ይሰለፋል፣ ሞትንም አይፈራም፡፡ ብእሲ ዘይሬኢ አክሊላቲሁ ኢይሜምእ፤ አክሊሉን የሚያይ ሰው ወደ ኋላ አያፈገፍግም በማለት እንዳስተማረን፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ተግሣጽ) ከፊቱ የሚጠብቀውን ክብርና ሽልማት የሚያስብ ተጋዳይ በአሁናዊ መከራው አይማረርም፡፡ መዝሙረኛው ዳዊት እንዲህ ይላል እለ ይዘርዑ በአንብዕ ወበሐሴት የዐርሩ፤ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ ወጾሩ ዘርዖሙ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ ወጾሩ ከላስስቲሆሙ፤ በልቅሶ(በዕንባ) የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ፤ በሄዱጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዷቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ እንዲል፡፡ (መዝ. ፻፳፭፥፮-፰)

በክረምት የሚዘራ ገበሬ ጠዋት ሲወጣ በላይ ዝናቡ ይወርድበታል፤ በታች ቅዝቃዜው፣ ጭቃውና ጎርፉ ይፈራረቁበታል፤ ስለዚህ በመከራ ይዘራል፡፡ የዘራው አፍርቶ አጭዶ ሲከምረው ግን መከራውን ረስቶ ጨምሬ ዘርቼ ቢሆን ኖሮ ይላል፤ እሸቱን እየበላ ነዶውን ሲሰበስብም ደስ ይለዋል፡፡ እንዲሁ በክርስትና ሕይወታቸው የጸኑ ሰማዕታት ከተሳለ ስለት፣ ከነደደ እሳት ሲገቡ መከራው ይሰማቸዋል፤ ጻድቃን ፍትወታት እኵያት ኃጣውእ ርኵሳት ሕሊናቸውን ያስጨንቃቸዋል፣ ድል ከነሡ በኋላ ግን ሰማያዊ አክሊልን ተቀዳጅተው በተድላ በደስታ ይኖራሉ፡፡

ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ በአካለ ነፍስ ሆኖ መነኮሳት በአክናፈ እሳት ወደ ኢየሩሳሌም ሲገቡ አይቶ አንድን አባት «ሰላም ለክሙ ብፁዓን መነኮሳት፤ ንዑዳን ክቡራን መነኮሳት ሆይ ሰላም ለእናንተ ይሁን»  አለው፡፡ መነኮሱም አንተም እንጂ ንዑድ ክቡር ነህ በዘመንህ ቀርነ ሃይማኖት ቆሞልሀልና አለው፡፡ ቆስጠንጢኖስም ይህንን አውቄስ ቢሆን መንግሥቴን ትቼ እንደ እናንተ በምናኔ በኖርሁ ነበር ብሎታል፡፡ (ፊልክስዩስ) ስለዚህ የዚህን ዓለም መከራና ሥቃይ የወዲያኛውን ክብር ያስረሳዋል፡፡ በዚህ ዓለም ሴት ልጅ በጭንቅና በምጥ ስትወልድ ታዝናለች ከወለደች በኋላ ግን ደስ ይላታል፤ ከወደለች በኋላ ግን ጭንቋንና ምጧን አታስበውም፤ ምክንያቱም ጨንቋንና ምጧን በልጇ ስለምትረሳው፡፡ (ዮሐ. ፲፮፥፳፩) ስለዚህ ክርስቲያኖችም የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ በተጋድሎና በትዕግሥት ሊያልፉት ይገባል፡፡ እንዲህም ከሆነ በሰው ኅሊና የማይተረጎም ሰማያዊ ክብርን ያገኛሉ፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወት አክሊልንም እሰጥሀለሁ እንዲል፡፡ (ራእ. ፫፥፲) ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት በተጋድሏቸውና በአሸናፊነታቸው ከሚቀበሉት ክብር አንጻር አሁን የሚያገኛቸው መከራ ኢምንት ነው፡፡ ስለዚህ ሰማያዊውን ክብር ለማግኘት መንፈሳዊውን ሩጫ መሮጥ ከኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር፡፡

ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል ሁለት

በዲ/ መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

የጾም ዓይነቶች

የጾም ዓይነቶች ሁለት ናቸው እነርሱም የአዋጅ እና የፈቃድ በመባል ይታወቃሉ፡፡

. የዐዋጅ ጾም

የዐዋጅ ጾም የሚባሉት በዐዋጅ ለሁሉም ሰው ማለት ከሰባት ዓመት በላይ ለሆነ ሰው ሁሉ የሚታወጅ እና በይፋ ሁሉም ተባብሮ ስለሚጾማቸው ነው፡፡ “በጽዮን መለከትን ንፉ፥ ጾምንም ቀድሱ፥ ጉባኤውንም አውጁ፥” (ኢዩ ፪፥፲፭) እንደተባለ አንዴ በቤተ ክርስቲያን ታውጆ ሥርዓት ተሠርቶለት የሚጾም ስለ ሆነ የአዋጅ ጾም ይባላል፡፡ የአዋጅ ጾም በማለት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምታውጃቸው እና ሁላችን በጋራ የምንጾማቸው አጽዋማት ሰባት ሲሆኑ እንደሚከተለው እንመለከታቸዋለን፡-

  1. ዓቢይ ጾም (ጾመ ሁዳድ)
  2. ጾመ ድኅነት (ዓርብ እና ረቡዕ)
  3. ጾመ ሐዋርያት (የሰኔ ጾም)
  4. ጾመ ፍልሰታ
  5. ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)
  6. ጾመ ነነዌ
  7. ጾመ ጋድ ናቸው፡፡

. የፈቃድ ጾም

የፈቃድ ጾም የሚባለው ሁሉም ሰው በዐዋጅ ሳይታዘዝ በፈቃዳችን የምንጾማቸው ናቸው፡፡ በቀኖና የሚሰጠን ጾም የሚመደበው ከዚህ ውስጥ ነው፡፡ አንዳዴም በተለየ ሁኔታ ለራሳችን የምንጾመው ጾምም የፈቃድ ይባላል፡፡ ለምሳሌ ጾመ ዮዲት (ጳጉሜን ላይ የሚጾም) እና ጾመ ጽጌ የሚጾሙ አሉ፤ እኒህም የፈቃድ አጽዋማት ናቸው፡፡

ውድ ተማሪዎች ጾም ፍቅርን ለእግዚአብሔር መግለጫ በመሆኑ ከልባችን ወደነው መጾም ይገባል፡፡ በጾም ስሜትን ራስን እንገዛበታለን፡፡ ጾም መንፈሳዊ ኃይልን ታጎናጽፋለች፤ አጋንንትን ለማራቅ እጅግ ትጠቅመናለች እንዲሁም ለመንፈሳዊ አገልግሎት የበረታን ታደርገናለች እና በአግባቡ በመጾም የምታሰጠውን ዋጋ ለማግኘት እንትጋ፡፡

እንደ ግብዞች አትጠውልጉ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዴት መጾም እንዳለብን የተራራውን ትምህርት ባስተማረበት ወቅት እንዲህ በማለት ተናገሮ እንመለከታለን “ስትጦሙም፥ እንደግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮)። በዚህ ንባብ ግብዞች የሚለውን ቃል በሁለት መልኩ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስቀምጦት ይገኛል። እነዚህም፡-

 ፩. መጦመቸው እንዲታወቅላቸው ፊታቸውን የሚያጠፉ እንዲሁም ይጠወልጋሉ። እነዚህ ጦማቸውን ዋጋ ለሚከፍል እግዚአብሔር ከማሳየት ይልቅ ለሰዎች አድናቆት ለማግኘት ሲሉ ብቻ የጾምን ዓላማ ያጠፉታል።

፪. ሳይጾሙ እንደጾሙ የሚያስመስሉ ከንፈራቸውን የሚያደርቁ ግብዝ ተብለው ተጠርተዋል። የምንጾመው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትን ለማድረግ ነው እንጂ ውዳሴ ከንቱን ለማግኘት አይደለም፤ በሁለቱም መልክ የተገለጡት ግብዞች ግን የጾምን ዓላማ የረሱና ያልተገነዘቡ ናቸው። በግብዝነት የሚገኘው ደስታ ጊዜያዊና ወዲያው የሚረሳ ነው ሆኖም ቅጣቱ ከባድ መሆኑን ዐውቆ መጠንቀቅ ይገባል።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በተለይ በልቶ ማስመሰል ውዳሴ ከንቱን መፈለግ ብቻ ሳይሆን ውሸትንም በውስጡ የያዘ ነውና ከግብዝነት በመራቅ በእውነት ለጾም ሕግና ሥርዓት ልንገዛ ይገባል። ለቤተሰብ ለጓደኛ ለቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ራሳችንን በውሸት ሕጋዊ አድርገን ለማሳየት ስንል መንግሥተ እግዚአብሔርን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይገባል። ለሰው ጾመኛ ከመምሰል በመታቀብ ዋጋ ለሚከፍለው ጌታ ራስን ማሳየት ያስፈልጋል። ፊትን በማጥቆር ከመጾም ፊትን ከእግዚአብሔር የሚያገኙትን ዋጋ በእምነት በተስፋ በመጠበቅ ብሩህ ማድረግ በእጅጉ ይገባል። ጌታችን ጾሞ እንዴት መጾም እንዳለብን አስገንዝቦናል በዚያው መሠረት በመጾም ሥርዓትን ልንፈጽም ይገባል።

ክርስቶስ አምላካችን ዐርባ ቀንና ሌሊት በመጾም ጾም የመልካም ሥራ መጀመሪያ እንድትሆን ሰጥቶናል። እኛም የሐዋርያቱን ትውፊትና ኑሮ መሠረት በማድረግ ያማረ የጾም ሕግን ከትውልድ ትውልድ እንቀባበለዋለን። ጌታችን የጾመው በቁዔት አገኝበታለሁ ብሎ ሳይሆን አጋንንትን፣ የኃጢአት ሥሮች የተባሉ ትዕቢት፣ ስስት እና ፍቅረ ነዋይን የምናሸንፍበትን ሕግ ሊሠራልን እና ተግባሩን ሊያመለክተን ነው እንጂ ጾማችሁን ሁሉ ጾሜላችኋለሁ ከዚህ በኋላ መጾም አይጠበቅባችሁም ለማለት አይደለም።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በግቢ ሕይወታችሁ ከብዙ ማኅበረሰብ ጋር እንደመኖራችሁ በሃይማኖት ከማይመስሉን በተለይ ከመናፍቃን ጥያቄ ሊቀርብልን ይችላል። ለምሳሌ አጽዋማት ለድኅነት አያስፈልጉም አንዴ ክርስቶስ ጾሞልናል፤ በዚህ ጊዜ እንድትጾሙ የተጻፈው የት ነው? ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም የሚለውን ሕግ ጥሳችኋል ሊሉን ይችላሉ።

ውድ ተማሪዎች ከመናፍቃን ጋር ያለን ልዩነት ሰፊና የመዳናችን መንገድ ላይ መሆኑን ልብ ማለት አለባችሁ ይህ ማለት ከላይ የጠቀስነው ንግግራቸው የሚመነጨው እምነት ብቻ ከሚለው አስተምሮአቸው ነው። ምግባር ለድኅነት አያስፈልግም በጸጋው ብቻ ድነናል ከሚለው አቋማቸው መሆኑን በመረዳት ከእነርሱ መራቅ ሐሳባቸውን አለመስማት ይኖርብናል። ምክንያቱም ጾም ትእዛዘ እግዚአብሔር ናት፤ ምግባር የእምነት ነፍስ ናትና “መጽሐፍም፦ አብርሃምም እግዚአብሔርን አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቈጠረለት ያለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ። ሰው በእምነት ብቻ ሳይሆን በሥራ እንዲጸድቅ ታያላችሁ። … ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደ ሆነ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው።” (ያዕ. ፪፥፳፫-፳፮) እንደተባለ። እምነት ከምግባር ተዋሕዶ ሊገኝ ግድ ነው። እንግዲህ ከምግባራት ቀዳሚዋ ጾም መሆንዋ ደግሞ ሊዘነጋ አይገባውም። ጌታችን ስለ ሆድ ማሰብ ሞት እንደሆነ አስተምሮናል አስቀድመን ማሰብ የሚገባን ስለ ጽድቅ መሆኑንም አሳስቦናል “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፥ ይጠግባሉና።” (ማቴ. ፭፥፮)። “ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?” (ማቴ. ፮፥፳፭)።

ስለዚህ ክርስቶስ ጾሞልሃል የሚለውን የሰይጣን ትምህርት ትተን “ከመዝ ግበሩ፤ እንዲህ አድቡ” የሚለውን የክርስቶስን ድምጽ በመስማት የተወልንን የአርአያነት መንገድ በመከተል እውነተኛ በጎቹ ልንሆን ይገባል። “ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል።” (ማቴ. ፮፥፴፫) “ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮።)  ‘ይህም ሁሉ’ የተባለው ምግብን እና መሰሎቹን ነው። ክርስቶስ አትጹሙ አላለም ስትጾሙ እንደ ግብዞች አትሁኑ በማለት አጿጿሙን ተናገረ እንጂ ስለዚህ ጾም ክርስቶሳዊ ትእዛዝ ነው።

ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም በማለት ሆድን አምላክ በማድረግ ሊሾሙብን እንደ ሔዋን ራቁታችን ሆነን ገነትን መንግሥተ ሰማይን አጥተን እንዳንጠፋ መጠንቀቅ አለብን።  ውድ ተማሪዎች ተመልከቱ ጌታችን ስለ እጅ ንጽሕና ሲጨነቁ ስለ አመጋገብ ወጋቸው ከሕገ መጽሐፍ በላይ ሲያሳስባቸው ተመልክቶ የተናገራቸውን ነገር “እርሱም፦ እናንተ ደግሞ እንደዚህ የማታስተውሉ ናችሁን? ከውጭ ወደ ሰው የሚገባ ሊያረክሰው ምንም እንዳይችል አትመለከቱምን? ወደ ሆድ ገብቶ ወደ እዳሪ ይወጣል እንጂ ወደ ልብ አይገባምና አላቸው። እርሱም አለ፦ ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው። ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ ሐሳብ፥ ዝሙት፥ መስረቅ፥ መግደል፥ ምንዝርነት፥ መጐምጀት፥ ክፋት፥ ተንኰል፥ መዳራት፥ ምቀኝነት፥ ስድብ፥ ትዕቢት፥ ስንፍና ናቸውና፤ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል ሰውን ያረክሰዋል።” (ማር. ፯፥፲፰-፳፫)። ተማሪዎች ተመለከታችሁን? ይህ ጾምን የሚያጸና እንጂ የሚሽር ነውን? አይደለም ምክንያቱም ጾም ማለት ከምግብና ከሚያረክሶ ነገሮች ሁሉ መራቅ ነው።

በአጠቃላይ ከመናፍቃን ራሳችንን እንጠብቅ በተዋበች የጾም ሕግ ጽድቅን እንፈልግ፤ ከተድላ ደስታ በመራቅ ከእግዚአብሔር ጋር አንድ እንሁን “ትእዛዙንም የሚጠብቅ በእርሱ ይኖራል እርሱም ይኖርበታል፤ በዚህም በእኛ እንዲኖር ከሰጠን ከመንፈሱ እናውቃለን።” (፩ኛዮሐ. ፫፥፳፬ እንደተባለ። በተጨማሪም ምሳሌውን አርአያነቱን በማስተዋል እንከተል “በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል።” (፩ኛዮሐ. ፪፥፮) ተብሎ እንደተጠቀሰ።

የአጽዋማትን ጊዜ የተመለከተውን ልንወዛገብበት አይገባም። ውድ ተማሪዎች የእኛ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሥርዓተ አምልኮ ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ አይደለም ይልቁንም የቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት፣ ትውፊትና ከሐዋርያት ጀምሮ ያሉ አበው ትምህርት ሕይወት እንደ ምንጭ የሚወሰድ በመሆኑ ከበቂ በላይ ማስረጃ አለን። በሐዲስ ኪዳን ቀኖና ውስጥ ያሉ ስምንቱ መጻሕፍት ሁሉም ላይ የጾም ጊዜ ሥርዓት በቀኖናው ተጽፎ እንደሚገኝ መዘንጋት አይገባም።  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Top of Form

Bottom of Form

Top of Form

Bottom of Form

ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል አንድ

በዲ/ መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

ጾም ለሰውነት የሚያምረውን እና የሚያስጎመዠውን ነገር ሁሉ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ብሎ  መተው፣ ራስን በመግዛት ጣዕመ ዓለምን በመናቅ እግዚአብሔርን መከተል ማለት ነው፡፡ ጾም  ራስን ከክፉ ሥራዎች ሁሉ በማሸሽ የመንፈሳዊ ተጋድሎ መፈጸሚያ መሣሪያ እና የሥጋ ልጓም ነው፡፡ መንፈሳዊ በረከትን ለማግኘት ለትእዛዘ እግዚአብሔር ራስን ማስገዛት ነው፡፡ ፍጹም የሆነ የእግዚአብሔርን ርዳታ ማግኛ የፍቅር መንገድ ነው፡፡ ጾም ሃይማኖትን መግለጫ በተግባር ማሳያ መታመኛ መሣሪያ ነው፡፡ ጾም፤ ወዶ ፈቅዶ ምግብን በጊዜ ገደብ ጥሉላትን በቀናት/በወራት ገደብ እንዲሁም ነፍስን ከሚያሳድፉ ክፉ ሥራዎች መከልከል ነው፡፡ ለእግዚአብሔር ያለን ፍጹም ፍቅር የሚገለጠው በጾም በጸሎት እና ምጽዋት ነው፡፡ የቀና እና የተስተካከለ መንፈሳዊ ሕይወትን ከሚያደናቅፉ ማናቸውም እኩይ ተግባራት መራቅ እና መከልከል ጾም ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ነፍስን ሊያቆስላት የሚችለው ምንድን ነው? ስንል መልሱ የሥጋ ፈቃድን መፈጸም፣ በደል፣ ኃጢአትነው የሚል ይሆናል፡፡ ሰው ተማሪ ቢሆን ሠራተኛም ቢሆን በምንም ዓይነት ሥራ እና ሁኔታ ላይ ቢሆን ክርስቲያናዊ ሕይወቱን ለማረም ዕለት ዕለት መንፈሳዊ ተግባራትን መተግበር ያስፈልጋል፡፡ በይበልጥ ሐዋርያት የሥራ መጀመሪያ ያደረጓትን ጾምን እኛም አጥብቀን ልንይዝ ይገባል፡፡ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፥ ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው።” (ሮሜ. ፰፥፮)፡፡ ሥራችንን ክርስቲያናዊ ጉዞአችንን ፍጹም የሚያደርግልን ጾም ነው፡፡ ለዚህም ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን እንደ ምሳሌ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ስለዚህ ተማሪዎች ቀዳሚት ትእዛዝ የሆነች ሕግን ገንዘብ በማድረግ ሕይወታችንን ሰማያዊ ዋጋ በሚያሰጥ መልክ እንምራ፡፡

ጾምን ለምን እንጾማለን?

ጾም በመጀመሪያ ለሰው የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ የሰው ልጅ ቢመራበት የዘላለምን ሕይወት የሚወርስበት ልዩ የእግዚአብሔር የፍቅር ሕግ ነው፡፡ ሰው ፍትወቱን በዚህች ባማረች ሕግ ገዝቶ ዓይኑን ክፉ ከማየት፣ ጆሮውን ክፉ ከመስማት፣ ምላሱን ክፉ ከመናገር ከማማት፣ እግሩን እጁን ከመስረቅ ደም ለማፍሰስ ወደ ክፉ ከመገስገስ ቢከለክል ዋጋው ምንኛ ያማር ይሆን ነበር፡፡ እኛ በዚህ ዘመን ያለን ወጣቶች በዓለሙ ካለ ክፋት የትኛውን ተጸይፈን እንተዋለን? ዘመነኛው ቴክኖሎጂ ያመጣልንን ማኅበራዊ ሚዲያ በመጠቀም ክፉኛ ወደሚያቆስለን ለገሃነም ወደሚሰጠን የሥጋ ሥራ አዘንብለናል፡፡ ነገር ግን የተሰጠንን በጎ አእምሮ በመጠቀም ወደ ኃጢአት ከመሄድ ራሳችንን ልንጠብቅ እና ልናነጻ ይገባል፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ የጾምን ጥቅም በቅደም ተከተል እንመልከት፡–  

. ኃይለ እግዚአብሔርን ለማግኘት

አብዝቶ መመገብ ፈቃደ ሥጋ በፈቃደ ነፍሳችን ላይ እንዲሰለጥን ሰፊ በር ይከፍታል፡፡ ፍትወታተ ሥጋ እንዲሰለጥኑብንም ዋነኛ ሞተራቸው በመሆን ይጠቀሳል፡፡ ጥጋብን፣ ትዕቢትን፣ ንዝህላልነትን፣ ዝሙትን በማምጣት መንፈሳዊ ፍሬን እንዳናፈራ ያግደናል፡፡ ሰዶምን በእሳት እንድትቃጠል ካደረጓት ምክንያቶች አንዱ እንጀራን መጥገብ እንደሆነ (ሕዝ. ፲፮፥፵፱) ተገልጧል፡፡ ፈቃደ ሥጋችን በፈቃደ ነፍሳችን ላይ ኃይል እንዳይኖረው ጾም መጾም እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነቢዩ ዳንኤል ከሦስቱ ሕፃናት ጋር ከኢየሩሳሌም ተማርከው ወደ ናቡከደነፆር ግዛት ከተወሰዱ ዕብራውያን ወጣቶች መካከል ተመርጦ ሦስት ዓመት በከለዳውያን ትምህርት ቤት የከለዳውያንን ጥንቆላ (ኮከበ ቆጣሪ) ሕልም መፍታት፣ ቋንቋ እና ባህላቸውን ከሦስቱ ወጣቶች ጋር በመሆን እንዲያጠኑ በተቃራኒው ደግሞ የራሳቸው የሆነውን የእስራኤልን እምነት እና ባሕል እንዲረሱ በተደረጉበት ጊዜ ዳንኤል እንዲመገቡ የተፈቀዱላቸውን የንጉሡን ምግብ እና መጠጥ ከመብላት እንቢ አለ፤ የአሕዛብ ምግብ እንደሚያረክሰው አስቧልና፡፡ ይልቁንም ቆሎ እየበሉ ይማሩ እንደነበር ትንቢተ ዳንኤል ያስገነዝበናል፡፡

ሰውነታቸው ቅቤን በማጣት ቢነጣም ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸው ኅብረት በጣም ከፍተኛ ነበር፡፡ በጾም መጠንከራቸው በትምህርታቸው ጎበዝ እና በንጉሥ ፊት ሞገስ ያላቸው የሚመረጡ ከመሆን አላገዳቸውም፤ እንዲያውም ከሌሎቹ በላይ ሞገስ እንዲኖራቸው በሀገሪቱ ውስጥ ሥልጣን እንዲያገኙ፣ የተደበቀን ምሥጢር በመግለጥ የበረቱ እንዲሆኑ አደረጋቸው እንጂ፡፡ እግዚአብሔርም በነገር ሁሉ ይረዳቸውና ከጎናቸው ይሆንላቸው እንደነበረ መጽሐፍ ያስገነዝበናል፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው በጾም በመጽናታቸው እና ከኃጢአት ራሳቸውን በመጠበቃቸው ባገኙት ኃይለ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ስለዚህ ወጣቶች (የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች) ስንጾም በትምህርታችን ልንደክም እንደምንችል እያሰብን እግዚአብሔር ከሚሰጠን ኃይል እና ጥበብ እንዳንርቅ ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡

ክርስቲያን መንፈሳዊ ተግባራትን በተመቸው ቀን ብቻ የሚተገብር አይደለም በጊዜውም ያለጊዜውም ጸንቶ የሚገኝ ነው እንጂ፡፡ ጾም ሌሎችን ምግባራት (ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት…) ለመፈጸም ፍጹም ኃይልን የምትሠጥ በጎ ተግባር ናት፡፡ የመንፈሳውያን ኃይል የሆኑትን ትዕግሥትን፣ ቸርነትን፣ በጎነትን፣ ራስን መግዛትንወዘተ ገንዘብ ለማድረግ ጾም ዋና መሣሪያችን ነው እና ገንዘብ እናድርገው፡፡

. ተጋድሎን መፈጸሚያ ነው

በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምንጋደለው ከመንፈሳውያን የክፋት ሠራዊት ጋር እንደሆነ እንዲህ በማለት ተነግሮናልመጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።” (ኤፌ. ፮፥፲፪)፡፡ ለመጋደል የተዘጋጀ ሰው ደግሞ መሣሪያ እንደሚያስፈልገው  ይታወቃል ስለዚህ ጾም ከሁሉ ቀድሞ የሚገኝ ተጋድሎ የመፈጸሚያ መሣሪያ ነው፡፡ በቀንና በሌሊት ከቤተ መቅደስ ሳይለዩ እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ያገለገሉ ቅዱሳን የክፋት ሠራዊትን ድል የማድረግ ኃይልን ተጎናጽፈዋል፡፡ ልባችን በጸጋ እንጂ በምግብ እንዳይጸና ሐዋርያው አስጠንቅቆናል፤ ምግብን አብዝቶ በመብላት እና ለምግብ በማድላት የተጎዳ እንጂ የተጠቀመ እንደሌለ አስተምሮናልና (ዕብ. ፲፫፥፱)፡፡

የተወደዳችሁ ተማሪዎች ተድላና ደስታን በመፈለግ መንግሥተ እግዚአብሔር አትወረስም፡፡ እስኪ ሊቀ ነቢያት ሙሴን እንመልከት ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከክርስቶስ ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መራብን መረጠ፡፡ በዚህ ምክንያት ከሞቀ መኖሪያ ከቤተ መንግሥት ለስደት ተዳረገ፤ ተራበም፤ ተጠማም የሚያገኘውን ዋጋ በዚያ ዘመን ሆኖ ተመልክቷልና (ዕብ. ፲፩፥፳፬፳፭)፡፡ ይህን በማድረጉ ተጎዳ ወይስ ተጠቀመ? በጣም ተጠቀመ እንጂ የተጎዳው አንዳች አልነበረም፡፡ ሙሴ ለዐርባ ቀናት ከምግብ በመከልከል ከእግዚአብሔር ጋር በመነጋገር ሕግጋትን ታቦትን ከአምላከ ቅዱሳን መቀበል የቻለው በጾም በመጋደሉ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ሰማይን እስከ መለጎም የደረሰ ሥልጣንን ማግኘት የቻለው ዐርባ ቀን እና ሌሊት ለመጾም ይከብድብኛል ሰውነቴ ይከሳል ሳይል ሳይፈራ በጾም በጸሎት በመቆሙ ከክፉዎች ጋር ባለመተባበሩ ነው፡፡ ስለዚህ በረጅሙ የክርስትና ጉዙአችን ውስጥ ጾም በጣም ወሳኝ ነገር መሆኑን ማሰብ እንደሚገባ ልንጋደል ይገባል፡፡ የሥጋችን ፈቃድ ለመግዛት በምናደርገው ተጋድሎ ውስጥ ጾም ጉልህ ሚና አለው፡፡ ጾም የነፍስን ቁስል ትፈውሳለች፤ የሥጋንም ፈቃድ ወይም ፍላጎት ዝም ጸጥ ታሰኛለች እና ለተጋድሎ ጠቃሚ መሣሪያ ናት፡፡

. እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመኖር

የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰው ሕያው ሆኖ እንዲኖር ነው፡፡ ማንም በሞት እንዲጠፋ ከገነት ከመንግሥተ ሰማይ እንዲጎድል አይፈልግም፡፡ የሰው ትልቁ ተስፋ መንግሥተ እግዚአብሔርን ወርሶ ዘለዓለማዊ መሆን ነው፡፡ የሕይወት መውጫው ልባችን እንደሆነ መጽሐፍ ይነግረናልአጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና።” (ምሳ. ፬፥፳፫) አዳም አባታችን አትብላ የምትለውን ሕግ በመሻሩ የሥጋ ፈቃዱን በመፈጸም ከፈቃደ እግዚአብሔር ርቆ በእግረ ሞት ተረግጧል፤ እኛም ከዚህ ሕግ ፈቀቅ ብንል የአዳም ዕጣ ሊገጥመን እንደሚችል ጥርጥር የለውም፡፡ ታዲያ ፈቃደ እግዚአብሔር እየፈጸምን ለመኖር ምን ያስፈልገናል? ካልን ራስን መግዛት የምታስችለውን ጾምን ገንዘብ ማድረግ ነው፡፡ (ኢዩ. ፪፥፲፪) በፍጹም ልብ በመጾም ወደ እርሱ እንድንመለስ መማጸኑ እግዚአብሔር የሚወዳት ጾም ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም የሚያስችል ትልቅ ኃይል እንዳላት ያመለክታል፡፡ ጾም በሰው ጥበብ የተጀመረች ሕግ አይደለችም ምን እንደምትጠቅም የሚያውቅ አምላክ ፈቃዱን እንድንፈጽምባት የሠራት ሕግ ናት እንጂ፡፡

በመጀመሪያ ከመጾማችን በፊት ጾም አድካሚ እና ጎጂ ሕግ ነው ብለን ከመሳት ራሳችንን ልንጠብቅ ይገባል፡፡ ይህ ሕግ የፍቅር ሕግ ነው፤ ከአምላካችን ጋር ኅብረት የምናደርግበት የምሕረት ዓይኑ እንድትመለከተን የምታደርግ ሕግ ስለሆነች በጾም ወደ ፈጣሪ መመለስን እንደ መጎዳት ማሰብ ፈጽሞ ስህተትን ያስከትላልና እንጠንቀቅ፡፡ ፈተና እየተፈተንም ቢሆን እያጠናን ልወድቅ እችላለሁ በሚል ፍርሃት አምላክን ከማሳዘን ከመንግሥቱ ከመጉደል መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡

በአጠቃላይ የክርስትና ዋና ዓላማ በእንግድነት በዚህ ዓለም ባለንበት ዘመን ከፈቃደ ሥጋ መራቅ፤ ነፍስና ሥጋን ማንጻትና የእግዚአብሔር ማደሪያ ማድረግ ነው። ይህ ደግሞ በብዙ ድካምና ተጋድሎ የሚሳካ ነው። በመጽሐፍ “. . . ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል።” (ሐዋ. ፲፬፥፳፪) እንደተባለ መንገዱ የተደላደለ ሳይሆን ብዙ ተጋድሎ የሚያስፈልገው መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል። ገዢዋ የሥጋ ፈቃድ የሆነባት ሰውነት ሞት ያገኛታልበገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፥ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘለዓለምን ሕይወት ያጭዳል።” (ገላ. ፮፥፰) እንዲል ሥጋን በጾም ለነፍስ ማስገዛት ሕይወትን ያስገኛል።

እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፤ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ። በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና። ” (ሮሜ. ፰፥ ፲፫፲፬) ጾም ፈጽሞ የሥጋ ሥራን ማስወገጃ፣ ተጋድሎን መፈጸሚያ መንገድ ነው።  “መብል ለሆድ ነው፥ ሆድም ለመብል ነው፤ እግዚአብሔር ግን ይህንም ያንም ያጠፋቸዋል። ሥጋ ግን ለጌታ ነው እንጂ ለዝሙት አይደለም፤ ጌታም ለሥጋ ነው” (፩ኛቆሮ. ፮፥፲፫) ሥጋዊ መብልን በመብላት የሚሠራ ጽድቅ የለም፤ ይልቁንም ብዙ ምግብ ለዝሙት፣ ለትዕቢት የሚያጋልጥ በመሆኑ በጾም ሰውነታችንን ከትዕቢት እንዲሁም ከዝሙት እንጠብቅ። ይህንን ካደረግን ከሆድ ጋር ከመጥፋት ራሳችንን እንታደጋለን። መንፈሳዊ ፍሬን ለማፍራት የምትቀድም ምግባር ጾም ናት ስለዚህ አጥብቀን እንፈልጋት እንያዛትም።የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችምና።” (ሮሜ. ፲፬፥፲፯) በጾም የምናገኛት ተስፋችን ምን እንደምትመስል በታወቀ ጊዜ ከምግብና ከክፋት በመራቅ የምንገባባት መሆኗንስ ተረዳን? ሰው ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ የሚያስፈልገው ጾም እንጂ ምግብ አይደለምመብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም፤ ባንበላም ምንም አይጎድለንም ብንበላም ምንም አይተርፈንም።” (፩ኛቆሮ. ፰፥፰) እንደተባለ። የምግብ ኃይል ለሥጋ ነው የጾም ኃይሏ ግን ለነፍስ ነውየክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑት ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ።” (ገላ. ፭፥፳) የተባለውን እናስተውል።

ይቆየን

 

ጾመ ነቢያት

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሰባት የዐዋጅ አጽዋማትን በቀናት፣ በሳምንታትና በወራት ቀምራ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ እንጠቀምበት ዘንድ ደንግጋ አበርክታለች፡፡ ከእነዚህ አጽዋማት መካከል ደግሞ ጾመ ነቢያት አንዱ ሲሆን ኦርቶዶክሳውያን ከኅዳር ፲፭ እስከ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ዋዜማ ድረስ የምንጾመው ጾም ነው፡፡  

እግዚአብሔር ለአዳም አባታችን በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ይህንን ዓለም ያድን ዘንድ የሰውን ሥጋ ለብሶ እንደሚወለድ ነቢያት በትንቢት መነጽርነት ተመልክተው ተናግረዋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፣ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፤ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” (ኢሳ. ፯፥፥፲፬) እንዲል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩከአጥቢያ ኮከብ አስቀድሞ ከሆድ ወለድሁህተብሎ እንደተጻፈው፡፡ (መዝ. ፻፱፥፫) በተጨማሪምእነሆ በኤፍራታ ሰማነው፤ ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው፤ እንግዲህስ ወደ እግዚአብሔር ማደሪያዎች እንገባለን፤ የጌታችን እግሮቹ በሚቆሙበት ቦታ እንሰግዳለን” (መዝ. ፻፴፩፥፮) በማለትይወርዳል፣ ይወለዳልየሚለውን የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይህን ዓለም ለማዳን በሥጋ መምጣት ተናግረዋል፡፡ ነቢያት በዚህ ብቻ ሳያበቁ ስለ ስደቱ፣ ስለ ጥምቀቱ፣ ወንጌልን ስለመስበኩ፣ መከራ ስለ መቀበሉ፣ ስለ ሞቱ፣ ስለ ትንሣኤው፣ ዕርገቱና ዳግም ምጽዓቱ በትንቢት ተናግረዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነቢያት የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መወለድ እየናፈቁ ጾመውታልና ጾመ ነቢያት ተብሏል፡፡

የነቢያት ትንቢት ፍጻሜውን አግኝቶ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜም የአዳም ተስፋው ተፈጽሟልናጾመ አዳምእየተባለም ይጠራል፡፡ የጾሙ መጨረሻም በዓለ ልደት በመሆኑጾመ ልደትይባላል፡፡ የነቢያት ትንቢት ተፈጽሞ ጨለማውን ዓለም በወንጌል ብርሃንነት (በስብከት) አጣፍጧልናጾመ ስብከትተብሎ ይጠራል፡፡

እንደዚሁም ሐዋርያት በዓለ ልደቱን እንዴት ዝም ብለን እናከብረዋለን? ነቢያት አባቶቻችንይወርዳል ይወለዳልብለው በተስፋ እየናፈቁ ጾመውታል፤ በዓለ ትንሣኤውን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብረዋለን፤ በዓለ ልደቱንም ጾመን በረከት እናገኝበታለን ሲሉ ጾመውታልናጾመ ሐዋርያትይባላል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን እንደምትፀንስ ካበሠራት በኋላ “ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?” በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ ጾማዋለችና ይህ ጾምጾመ ማርያምእየተባለም ይጠራል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በነቢያት ጾም ነቢያት፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ሐዋርያት፣ ጻድቃን ሰማዕታት ጾመው በረከት አግኝተውበታልና እኛ ምእመናንም በረከትን እናገኝ ዘንድ መጾም እንደሚገባን የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ ጾመን፣ ጸልየን የበረከቱ ተሳታፊዎች ያድርገን፡፡ አሜን፡፡  

ምንጭ፡

ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡

ጾምና ምጽዋት፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯፶፡፡

 

የዳረጎት ዕጣዎች

ማኅበረ ቅዱሳን ከግንቦት ፩ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ጀምሮ ሲያሠራጨው የነበረው የገቢ ማሰባሰቢያ ትኬት  ኅዳር ፳፩ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም ዕጣ ማውጣቱ ይታወቃለል፡፡ በዚህም መሠረት ፳፩ የዳረጎት ዕጣዎች የወጡ ሲሆን ዐሥር የዕጣዎች እያንዳንዳቸው የሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ፤ እንዲሁም ዐሥራ አንድ ዕጣዎች እያንዳንዳቸው መዝሙረ ዳዊት የሚያስገኙ ሆነው ወጥተዋል፡፡  

በዚህም መሠረት የሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስገኙት ዕጣዎች፡-

  • 373427
  • 360509
  • 345974
  • 249715
  • 263391
  • 435703
  • 320085
  • 394074
  • 315800
  • 232590

ዐሥራ አንድ የመዝሙረ ዳዊት የጸሎት መጽሐፍ የሚያስገኙት ዕጣዎች፡-

  • 374223
  • 354749
  • 247657
  • 265287
  • 317331
  • 435060
  • 319033
  • 291453
  • 179959
  • 259285
  • 244216 ሆነው ወጥተዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የባለ ዕድለኞች ዕጣ ቁጥሮችን ይፋ አደረገ

ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎትን ለማጠናከር ይረዳው ዘንድ “ዘመኑን የዋጀ ንቁ ትውልድ ለቤተ ክርስቲያን” በሚል መሪ ቃል ለአባላት፣ ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና አገልግሎቱን ለሚደግፉ ምእመናን ሲያሠራጭ የቆየው ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም፣ ወደ ግብጽና ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝትን ጨምሮ ሌሎችንም ዕድሎችን የሚያስገኙት የበረከት የዕጣ ቁጥሮች በቴክኖሎጂ በታገዘ የዕጣ አወጣጥ መርሐ ግብር ታዛቢዎችና ምእመናን በተገኙበት ኅዳር ፳፩ ቀን ፳፳፻፲፰ ዓ.ም ይፋ አደረገ፡፡  

በዕጣ አወጣጥ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ መምህር ዋሲሁን በላይ ባስተላለፉት መልእክት “ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በተሻለ ጥራትና አቅም ለማስተማር ብቻውን ሳይሆን የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ፣ የሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የመምህራንና የምእመናን ትብብርና ድጋፍ ሳይለየው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በተሻለ ጥራትና አቅም አገልግሎቱን እየሰጠ ይገኛል” በማለት የገለጹ ሲሆን የበረከት ዕጣ ትኬቱን በማሠራጨት ሂደት ውስጥ የተሳተፉትን ሁሉ አመስግነዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ አበበ በዳዳ የበረከት ዕጣ ትኬቱ የተዘጋጀበት ምክንያትና ሂደቱን በተመለከተ ባስተላለፉት መልእክት “ማኅበረ ቅዱሳን ከ፲፱፻፹፬ ዓ.ም ጀርሮ በቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠው ፈቃድና ኃላፊነት መሠረት  የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ለማስተማር መምህራንን በመመደብ፣ መማሪያ ቦታን በማዘጋጀት፣ በንስሓ አባቶች አማካይነት ሕይወታቸውን በመንፈሳዊ መንገድ እንዲመሩ በማድረግ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ኦርቶዶክሰውያን ተማሪዎችን በማፍራት አስመርቋል፡፡ “በዚህም አገልግሎት ተማሪዎች ለራሳቸው፣ ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ አገልግሎት እያበረከቱ ይገኛሉ፡፡” ብለዋል፡፡

አቶ አበበ አያይዘውም “ማኅበረ ቅዱሳን ከ፲፱፩፺፮ ዓ.ም ጀምሮም ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ሲያስተምር በየጊዜው የሚታዩ ክፍተቶችን በማረም በ፳፻፮ ዓ.ም በዓለማችን፣ በሀገራችንና በቤተ ክርስቲያን በሚታዩ ተለዋዋጭ ሁኔታዎች፣ የሰ/ት ት/ቤቶች ከ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ሥርዓተ ትምህርት መዘጋጀት፣ ማኅበረ ቅዱሳን ከ፳፻፲፮ ዓ.ም የተቋማዊ ለውጥ ትግበራ መጀመርና የመንግሥት የትምህርት ፖሊሲ መቀያየር ከግምት ውስጥ በማስገባት ከዐሥር ዓመታት በኋላ በ፳፻፲፯ ዓ.ም ለግቢ ጉባኤያት ሲሰጠው የነበረውን ሥርዓተ ትምህርት ከግምት ውስጥ በማስገባት መከለስ ችሏል” ሲሉ ገልጸዋል፡፡

“እነዚህም ምክንያቶችን መሠረት በማድረግ ፲፬ የትምህርት ዓይነቶች የተዘጋጁ ሲሆን ለኅትመት፣ የመምህራንን አቅም፣ ጥራትና ቁጥር ለማሳደግ፣ የመማሪያ ቦታ ችግሮችን ለመቅረፍና የሥልጠና መስጫ መእከል ለመገንባት ታስቦ የበረከት ዕጣው ተዘጋጅቷል” በማለት አብራርተዋል፡፡

በበረከት ዕጣ ትኬቱ አቅማቸውን ሁሉ በመጠቀም ድጋፍ ላደረጉና በማሠራጨት ለተባበሩት አካላት ሁሉ ምስጋና በማቅረብ የዕጣ መውጣት መርሐ ግብሩ እንዲጀመር አድርገዋል፡፡ በዚህም መሠረት፡-

፩ኛ ዕጣ፡- 409652፡- ወደ ኢየሩሳሌሌም ገዳማት ጉዞ ለ፯ ቀናት፣  

፪ኛ ዕጣ፡- 309903፡- ወደ ግብጽ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝት ለ፯ ቀናት፣

፫ኛ ዕጣ፡- 076840፡- ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት ወደ አንዱ ከአንድ ቤተሰብ ጋር መንፈሳዊ ጉብኝነት በአውሮፕላን ለ፭ ቀናት፣

፬ኛ ዕጣ፡- 366930፡- ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝት ከሁለት ቤተሰብ ጋር በየብስ ትራንስፖርት ለ፯ ቀናት፣

፭ኛ ዕጣ፡- 160582፡- ላፕቶፕ ኮምፐዩተር core i7 10Th G የሚያስገኘው የዕጣ ቁጥር፣

፮ኛ ዕጣ፡- 201414፡- ላፕቶፕ ኮምፒዩተር core i5 የሚያስገኘው የዕጣ ቁጥር፣

፯ኛ ዕጣ፡- 478450፡- ሳምሰንግ ታብሌት ጋላክሲ (Samsung Galaxy tablet A8 10.5) ሆነው ወጥተዋል፡፡

ኅዳር ጽዮን

በዓለ ሢመቱ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል

በዲ/ን አብርሃም

ኅዳር ፲፪ ቀን ንዑድ ክቡር የሆነ ለፍጥረቱ ሁሉ የሚማልድ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል የተሾመበት ዕለት ነው። የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍት “ኅዳር ፲፪ በዚህች ቀን ለሰው ወገን የሚያዝንና የሚራራ በእግዚአብሔር ጌትነት ፊት ሁል ጊዜ በመቆም ለፍጥረቱ ሁሉ የሚማልድ የመላእክት አለቃቸው ለሆነ ለቅዱስ ሚካኤል የበዓለ ሢመቱ መታሰቢያ ነው።” (መጽሐፈ ስንክሳር ኅዳር ፲፪፤ ድርሳነ ሚካኤል ዘኅዳር) በማለት ይገልጻሉ፡፡

ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‘ሚ’- ‘መኑ’፣ ‘ካ’- ‘ከመ’፣ ‘ኤል’- ‘አምላክ’ ማለት ሲሆን በአንድነት ሲነበብ “መኑ ከመ አምላክ፤ እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?” ማለት ነው። እግዚአብሔር መልእክትን በፈጠረ ጊዜ ሳጥናኤልን የመላእክት ሁሉ አለቃቸው አድርጎ ሹሞት ነበር። ነገር ግን ሳጥናኤል ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ክብር ትቶ አምላክነትን በመሻቱ በትዕቢቱ ምክንያት ሥልጣኑን ገፍፎ ወደ ጥልቁ ጥሎታል፤ በቦታውም ቅዱስ ሚካኤልን ሹሞታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህን ምክንያት በማድረግ ኅዳር ፲፪ ቀን በየዓመቱ በዓለ ሢመቱን ታክብራለች።

ደጉ እና ሩኅሩኁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በስሙ ለተማጸንን ሁሉ ከእግዚአብሔር የሚያማልደን ምሕረትን የሚያሰጠን መልአክ ነው ”ተውህቦ ምሕረት ለሚካኤል” እንዲል (ሥርዓተ ቅዳሴ)። ቅዱስ ሚካኤል ለፍጥረታት ሁሉ የሚራዳና የሚያዝን በእግዚአብሔር ፊት የሚቆምልን የምሕረትና የሰላም መልአክ ነው። “በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል” (ዳን. ፲፪፥፩) ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤል ‎የቅዱስ ሚካኤልን ክብር ሲገልጥ ይህንን ብሎ ብቻ አልቀረም “ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ” በማለት እኛ የአዳም ልጆች ዲያብሎስ ባዘጋጀልን መሰናክል እንዳንወድቅ የሚረዳን መልአክ እንደሆነ ይናገራል፡፡ (ዳን. ፲፥፲፫)

“ቅዱስ ሚካኤል ሆይ የያሬድ ልጅ ሄኖክ እንደጻፈው። ከልዑል ስም አጠራር ጋር ለተባበረ ስም አጠራርህ ሰላም እላለሁ። የእግዚአብሔር የምክሩ አበጋዝ ሆይ የተቸገሩትን የተጨነቁትን ዘወትር እንደምትረዳቸው ሁሉ እኔንም ለመርዳት ክንፍህን ዘርግተህ ፈጥነህ ድረስልኝ።” በማለት የቅዱስ ሚካኤልን ተራዳኢነት ይገልጻል፡፡ (መልክአ ሚካኤል)

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት የቅዱስ ሚካኤልንና የሌሎች መላእክትን ክብርና አገልግሎት ሲገልጥ “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።”‎ (መዝ. ፴፫፥፯) እንዲል ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን በሚፈሩ ሰዎች ዙሪያ ሁል ጊዜ ይከባሉ፤ ከሰይጣን ፈተና፣ ከረኃብ፣ ከችግር፣ ከመከራ ሁሉ ያድኑናል። ማዳናቸውም የክርስቶስን የማዳን ሥራ የሚተካከል አይደለም፤ እርሱ በሰጣቸው ጸጋ ከእርሱ ዘንድ ይቅርታንና ምሕረትን በማሰጠት የሚያድኑን ናቸው እንጂ።

ቅዱስ ሚካኤል አርምሞንና ትዕግሥትን የሚያስተምረን መልአክ ነው። “የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እንኳን ስለ ሙሴ ሥጋ ከሰይጣን ጋር በተከራከረ ጊዜ የስድብ ቃልን ሊናገር አልደፈረም፤ ‘እግዚአብሔር ይገስጽህ’ አለው እንጂ” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ (ይሁዳ ፩፥፱)

የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤል ጥበቃው አይለየን! ከበዓሉ በረከት ይክፈለን!