የትንሣኤ ትሩፋቶች

ከመምህር ተፈሪ መንገሻ


የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የክርስትና እምነት መሠረትና የሰው ልጅ ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገረበት የድል አዋጅ ነው።

ከትንሣኤ እስከ ዕርገት ያሉት አርባ ቀናት እንዲሁም እስከ በዓለ ኀምሳ ያሉት ዐሥር ቀናት ቤተክርስቲያን የተመሠረተችባቸውና ሰማያዊው ሥርዓት ለሐዋርያት የተሰጠባቸው ልዩ ወቅቶች ናቸው። ፅንስ በማሕፀን እስከ አርባ ቀን ድረስ ተሥዕሎ መልክእ እንደሚሰጠው ክርስቶስም በሐዋርያት ልብ ቤተክርስቲያንን እየሣለላቸው ነበር።
​ጌታችን በዚህ የክብር ወቅት በመካከላቸው እየተገኘ ለሐዋርያቱ የገለጠላቸው ምሥጢራት፣ የሰጣቸው ተስፋዎችና የመሠረታቸው ሥርዓቶች ዛሬ ለምንኖርባት ቤተክርስቲያን ሕይወትና እስትንፋስ ናቸው። እነዚህ ነጥቦች ትንሣኤው ለዓለም ያበረከተውን ፍሬና ጌታችን በነዚህ ዕለታት የፈጸማቸውን ዓበይት ተግባራት ናቸው።

እነርሱም፦

  1. ሞትን አሸንፎ ከሙታን መነሣት
    ይህ የወርኀ ትንሣኤ መሠረት ነው። ጌታ በሦስተኛው ቀን ከመቃብር ተነሣ፣ ሞት የመጨረሻ አለመሆኑን አሳየ። ሞት በክርስቶስ ፊት ተሸነፈ፣ የሰው ተስፋ ከመቃብር በላይ እንዳለ ገለጠ። (ማቴ. ፳፰፥፩-፮፣ ፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፶፬-፶፯)
  2. ለሴቶች የትንሣኤውን ዜና በመጀመሪያ ማስታወቅ
    የሞት ምክንያት ቅድሚያ ሴቶች ቢሆኑ አሁን የትንሣኤውን ዜና ቀድሞ ለእነሱ ተነገረ። “ለማርያም መግደላዊት መጀመሪያ ታያት” (ማር. ፲፮፥፱) እንዲል።
    እንዲሁም መልአኩ ለሴቶቹ “ተነሥቶአል” ብሎ አበሠረ፤ ጌታም በመንገድ ላይ ተገልጦ “ደስ ይበላችሁ” አላቸው። ይህም እግዚአብሔር የመድኃኒቱን ዜና ወደ ደካሞችና በልብ ኀዘን ለተጎዱ ሰዎች እንደሚያመጣ ያሳያል። ማቴ. ፳፰፥፭-፲
    በዚህም ሴቶችን የትንሣኤው ቀዳሚ ምስክሮች በማድረግ ክብራቸውን አድሷል።
  3. የሰላም አዋጅን ማወጅ
    ​ደቀ መዛሙርቱ በአይሁድ ፍርሃት ደጆቻቸውን ቆልፈው ሳለ፣ ጌታ በመካከላቸው በመቆም ‘ሰላም ለእናንተ ይሁን’ አላቸው” (ዮሐ. ፳፥፲፱)
    የዚህም ምክንያት ከትንሣኤው በፊት የነበረውን የፍርሃትና የጭንቀት መንፈስ በሰማያዊ ሰላም ለመተካት ነው።
  4. የመጻሕፍትን ምሥጢር መግለጥ
    ​ወደ ኤማሁስ ይጓዙ ለነበሩት ሁለት ደቀ መዛሙርት (ሉቃስና ቀለዮጳ) ስለ እርሱ የተጻፈውን ከመጻሕፍት እያነሣ ተርጉሞላቸዋል። “ከሙሴና ከነቢያት ሁሉ ጀምሮ ስለ እርሱ በመጻሕፍት ሁሉ የተጻፈውን ተረጎመላቸው” እንዲል። (ሉቃ. ፳፬፥፳፯)
    የዚህም ​ምክንያት ትንሣኤው ድንገተኛ ክስተት ሳይሆን፣ የነቢያት ትንቢት ፍጻሜ መሆኑን ለማስረዳት ነው።
  5. ምሥጢረ ቁርባንን ማጽናት
    ​በኤማሁስ መንገደኞች በቤት እንጀራውን ባርኮና ቆርሶ በመስጠት፣ በምሥጢረ ቁርባን በኩል የሚገኘውን የሱን መገኘት አስተምሯል።
    ​ “እንጀራውን አንሥቶ ባረከው፣ ቆርሶም ሰጣቸው፤ ዓይናቸውም ተከፈተ አወቁትም” (ሉቃ. ፳፬፥፴-፴፩) እንዲል።
    የዚህም ​ምክንያት በአካል ተለይቶ ካረገ በኋላ፣ በምሥጢረ ቁርባን አማካኝነት ከምእመናን ጋር ለዘላለም እንደሚኖር ለማሳየት ነው።
  6. የጥርጣሬን ግድግዳ ማፍረስ
    ​ለቶማስ ቁስሉን እንዲዳስስ በመፍቀድ፣ ትንሣኤው በመንፈስ ብቻ ሳይሆን በአካል (In the Flesh) መሆኑን አረጋግጧል። “ከዚያም በኋላ ቶማስን፦ ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን አለው።” እንዲል። (ዮሐ. ፳፥፳፯)
    የዚህም ​ምክንያት ትንሣኤውን ምትሐት ነው የሚሉ የሐሰት ትምህርቶች እንዲነሡ ያውቃልና ምክንያት ለማሳጣት ነው።
  7. የክህነት ሥልጣንን መስጠት
    ​ሐዋርያትን “እፍ” በማለት መንፈስ ቅዱስንና ኃጢአትን የመፍታትና የማሰር ሥልጣን ሰጥቷቸዋል። “ይህንም ብሎ እፍ አለባቸውና፦ መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ። ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል አላቸው። (ዮሐ. ፳፥፥፳፪)
    በዚህም ጌታችን የቤተክርስቲያን አስተዳደራዊና መንፈሳዊ መሪነትን (Hierarchy) መሥርቷል
  8. የተስፋና የንስሓ ሥርዓትን ማሳየት
    ​ጌታን ክዶት ለነበረው ለጴጥሮስ ሦስት ጊዜ “ትወደኛለህን?” ብሎ በመጠየቅ ወደ ቀደመ ማዕረጉ መልሶታል። “በጎቼን አሰማራ… ግልገሎቼን ጠብቅ” (ዮሐ. ፳፩፥፲፭-፲፯) ብሎም ሐዋርያነቱን አጽንቶለታል።
    ​አንድ ምእመን ኃጢአት ቢሠራ ተስፋ ቆርጦ እንዳይለይ በቤተክርስቲያን ውስጥ ንስሓ የገባ ማንኛውም ኃጢአተኛ ወደ ክብሩ ሊመለስ እንደሚችል በተግባር ለማሳየት ይህንን አድርጓል።
  9. መጽሐፈ ኪዳንንና የሥርዓተ አምልኮ ደንቦችን ማስተማ
    ​በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ትውፊት፣ ጌታ በእነዚህ ቀናት ሐዋርያትን “መጽሐፈ ኪዳን” አስተምሯቸዋል።
    “ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ነገር እየነገራቸው አርባ ቀን ታያቸው” (ሐዋ. ፩፥፫) እንዲል።
    ​ምክንያቱም ሐዋርያት ዓለምን በሚያስተምሩበት ጊዜ እንዴት ማምለክና ምን መጸለይ እንዳለባቸው ግራ እኔዳይገባቸውና ወጥ የሆነ የሥርዓተ ቅዳሴና የሃይማኖት መመሪያ እንዲኖራቸው ለማድረግ ነበር። ቅዱስ ጳውሎስ “ነገር ግን ሁሉ በአገባብና በሥርዓት ይሁን።” እንዳለው። ፩ኛ ቆሮ. ፲፬፥፵
  10. ዓለም አቀፍ የወንጌል ተልእኮ መስጠት
    ​ቤተክርስቲያን ከአይሁድ ተሻግራ ለአሕዛብ ሁሉ እንድትደርስ ትእዛዝ ተሰጥቷታል።
    “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” እንዲል። (ማቴ. ፳፰፥፲፱)
    የዚህም ​ምክንያት የክርስትና ሃይማኖት/ቤተክርስቲያን ወሰን ገደብ የሌለባት ዓለም አቀፋዊት (Universal) መሆኑን ለማወጅ ነው።
  11. ወደ ሰማይ ማረጉና ዳግም የመምጣቱን ተስፋ ማጽናት
    ​በመጨረሻም በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ባረገ ጊዜ፣ ዳግመኛ እንደሚመጣና እስከ ዓለም ፍጻሜ አብሯቸው እንደሚሆን ተስፋ ሰጥቷል። “እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” (ማቴ. ፳፰፥፳) እንዲል።
    ​በዚህም ጌታ ሐዋርያትና ተከታዮቻቸው በአሰቃቂ ስደትና መከራ ውስጥ ሲያልፉ ይህ ተስፋ እንዲያበረታቸው ነው።
  12. በበዓለ ኀምሳ መንፈስ ቅዱስን መላክ
    በዐሥረኛው ቀን (ከትንሣኤ በ፶ኛው ዕለት) ጌታችን በሰጠው ተስፋ መሠረት መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያት ላይ ወርዷል። “በዓለ ኀምሳ የተባለውም ቀን በደረሰ ጊዜ… እንደ እሳት የተከፋፈሉ ልሳኖች ታዩአቸው፤ በያንዳንዳቸውም ላይ ተቀመጡባቸው። በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው።” እንዲል። (ሐዋ. ፪፥፩-፬)
    ይህም የሆነበት ምክንያት
    ➜ ኃይልን ለመስጠት፦ ሐዋርያት ዓለምን ዞረው ወንጌልን እንዲያስተምሩ ከላይ የሚመጣ ሰማያዊ ኃይል ያስፈልጋቸው ስለነበር።
    ➜ ​ቤተክርስቲያንን ለመመሥረት፦ በዕለተ ጰንጤቆስጤ (በዓለ ኀምሳ) በቅዱስ ጴጥሮስ ስብከት ሦስት ሺህ ሰዎች ተጠምቀው የቤተክርስቲያን ጉዞ በይፋ የተጀመረበት ዕለት ስለሆነ።
    ➜ ​ቋንቋን ለመቀደስ፦ የሰው ልጅ በባቢሎን ግንብ ምክንያት ተከፋፍሎ የነበረውን ቋንቋ (ዘፍ. ፲፩) በመንፈስ ቅዱስ አንድነት አማካኝነት ለወንጌል አገልግሎት እንዲውል ለማድረግ ነው።
    ማጠቃለያ
    እነዚህ ሁሉ ከላይ የተመለከትናቸው ሁነቶች የጌታችን ትንሣኤን ተከትለው የመጡ የትንሣው ትፋቶች ናቸው።
    የጌታችን ትንሣኤው ባይገለጥ
    ➡️ ሐዋርያት ለ፫ ዓመት ከ፫ ወር የተማሩት ትምህርት ተረት ሆኖ ይቀር ነበር። ➡️ደቀ መዛሙርቱ በቀቢጸ ተስፋ እንደተበተኑ ይቀሩ ነበር።
    ➡️የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነቱ አይረጋገጥም ነበር።
    ➡️ሞት አስፈሪነቱ እንደቀጠለ ይኖር ነበር።
    ➡️ደቀ መዛሙርቱ ወንጌልን ለዓለም የመስበክ ወኔ አይኖራቸውም ነበር።
    ➡️መጽሐፈ ኪዳን መማር አይኖርም ነበር።
    ➡️የአግብኦተ ግብር ተግባር አይስተዋለም ነበር።
    ➡️የዕርገት በዓልን አናይም ነበር።
    ➡️የጰራቅሊጦስ በዓልን አናከብርም ነበር።
    እነዚህ በተጨባጭ ዛሬ ለእኛ ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የሚያስረዱን ነገር ቢኖር፣ በስንፍና፣ በቸልተኝነት፣ በግዴለሽነት፣ በሱስ፣ አጠቃላይ በኃጢአት ሞት ሞተን በተስፋ፣ ጊዜያችንን በአግባቡ ተጠቅመን ጠንክረን በመማር፣ በወንጌል እንዲሁም በንስሓ ትንሣኤያችን ካላረጋገጥን የሥጋ ተድላ ደስታ የነፍስ ድኅነትን ማግኘት አይታሰብም።
    የጌታችን ትንሣኤና ተከታዮቹ አምሳ ቀናት የታሪክ ለውጥ ብቻ ሳይሆኑ፣ የሰው ልጅ ተስፋ የታደሰባቸውና የቤተክርስቲያን መሠረት የተጣለባቸው የድል ቀናት ናቸው። ትንሣኤው ሞትን ድል ማድረግ ብቻ ሳይሆን አዲስ ሕይወትን፣ አዲስ ተስፋንና አዲስ ሥርዓትን እንዲሁም ሙሉና ሕያው የሆነችውን የክርስቶስን አካል (ቤተክርስቲያንን) ለሰው ልጅ የሰጠበት ታላቅ ምሥጢር ነው።
    ስብሐት ለእግዚአብሔር

ቅዳሜ

ቅዳሜ

ከመምህር አዲሱ በዛብህ

የትንሣኤ ሳምንት ቅዳሜ ቅዱሳት_አንስት_ይባላል።

በወንጌል ተጽፎ እንደምናነበው ፍቅሩን በማሰብ ጨለማውን ሳይፈሩ ወደ መቃብር ስለመጡት መግደላዊት ማርያም እና ማርያም ባውፍልያ በስፋት ቤተክርስቲያን እንድናስብ ስለምታስተምረን ቅዱሳት አንስት ተብሏል።

ወንጌሉ ስለዚህ ዕለት እንዲህ ብሎ ይገልጻል: – “ከሳምንቱም በፊተኛው ቀን መግደላዊት ማርያም ገና ጨለማ ሳለ ማለዳ ወደ መቃብር መጣች ድንጋዩም ከመቃብሩ ተፈንቅሎ አየች።እየሮጠችም ወደ ስምዖን ጴጥሮስና ኢየሱስ ይወደው ወደ ነበረው ወደ ሌላው ደቀ መዝሙር መጥታ፦ ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም አለቻቸው።

“ስለዚህ ጴጥሮስና ሌላው ደቀ መዝሙር ወጥተው ወደ መቃብሩ ሄዱ። ሁለቱም አብረው ሮጡ፤ ሌላው ደቀ መዝሙርም ከጴጥሮስ ይልቅ ፈጥኖ ወደ ፊት ሮጠና አስቀድሞ ከመቃብሩ ደረሰ፤ ዝቅም ብሎ ቢመለከት የተልባ እግሩን ልብስ ተቀምጦ አየ፥ ነገር ግን አልገባም። ስምዖን ጴጥሮስም ተከትሎት መጣ ወደ መቃብሩም ገባ፤ የተልባ እግሩን ልብስ ተቀምጦ አየ፥ ደግሞም በራሱ የነበረውን ጨርቅ ለብቻው በአንድ ስፍራ ተጠምጥሞ እንደ ነበረ እንጂ ከተልባ እግሩ ልብስ ጋር ተቀምጦ እንዳልነበረ አየ። በዚያን ጊዜ አስቀድሞ ወደ መቃብር የመጣውም ሌላው ደቀ መዝሙር ደግሞ ገባ፥ አየም፥ አመነም፤ ከሙታን ይነሣ ዘንድ እንዲገባው የሚለውን የመጽሐፉን ቃል ገና አላወቁም ነበርና። ደቀ መዛሙርቱም ወደ ቤታቸው ደግሞ ሄዱ።

“ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ በስተ ውጭ ቆማ ነበር። ስታለቅስም ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች፤ ሁለት መላእክትም ነጭ ልብስ ለብሰው የኢየሱስ ሥጋ ተኝቶበት በነበረው አንዱ በራስጌ ሌላውም በእግርጌ ተቀምጠው አየች።

“እነርሱም፦ አንቺ ሴት፥ ስለ ምን ታለቅሻለሽ? አሉአት። እርስዋም፦ ጌታዬን ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አላውቅም አለቻቸው። ይህንም ብላ ወደ ኋላ ዘወር ስትል ኢየሱስን ቆሞ አየችው፤ ኢየሱስም እንደ ሆነ አላወቀችም።

“ኢየሱስም፦ አንቺ ሴት፥ ስለ ምን ታለቅሻለሽ? ማንንስ ትፈልጊያለሽ? አላት።

“እርስዋም የአትክልት ጠባቂ መስሏት፦ ጌታ ሆይ፥ አንተ ወስደኸው እንደ ሆንህ ወዴት እንዳኖርኸው ንገረኝ እኔም እወስደዋለሁ አለችው።

“ኢየሱስም፦ ማርያም አላት። እርስዋ ዘወር ብላ በዕብራይስጥ፦ ረቡኒ አለችው፤ ትርጓሜውም፦ መምህር ሆይ ማለት ነው።

“ኢየሱስም፦ ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ፦ እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ ዐርጋለሁ ብለሽ ንገሪአቸው አላት።

መግደላዊት ማርያም መጥታ ጌታን እንዳየች ይህንም እንዳላት ለደቀ መዛሙርቱ ነገረች።” (ዮሐ. ፳፥፩-፲፰)

የሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት ስም ዝርዝራቸውንና መታሰቢያ ቀናቸው፤

ተ.ቁስምየመታሰቢያ ቀናቸው
1  ኤልሳቤጥ            የካቲት 16 
2  ሐናመስከረም 7 ቀን
3  ቤርዜዳን ወይም ቤርስትታኀሣሥ 10 ቀን
4  መልቲዳን ወይም ማርናጥር 4 ቀን 
5 ሰሎሜግንቦት 25 ቀን    
6 ማርያም መግደላዊትነሐሴ 6 ቀን
7 ማርያም እንተ ዕፍረት እኅተ አልዓዛርየካቲት 6 ቀን
8 ሐና ነቢይትየካቲት 20 እና ጥቅምት 6 ቀን
9 ማርያም እሞሙ ለደቂቀ ዘብዴዎስጥር 18 ቀን
10 ሶፍያ (በርበራ)ጥር 30 ቀን
11 ዮልያና (ዮና)ኅዳር 18 ቀን
12 ሶፍያ (መርኬዛ)ጥር 30 ቀን      
13 አውጋንያን (ጲላግያ)ጥቅምት 11 ቀን
14 አርሴማግንቦት 11 ቀን         
15 ዮስቲናጥር 30 ቀን              
16 ጤግላነሐሴ 6 ቀን                
17 አርኒ (ሶፍያ)ኅዳር 10 ቀን    
18 ዕሌኒጥር 29 ቀን                
19 ኢዮጰራቅሊያ መጋቢት 26 እና ነሐሴ 2 ቀን  
20 ቴዎክላ (ቴኦድራ)ጥር 4 ቀን        
21 ክርስቲያና (አጥሩኒስ)ኅዳር 18       
22 ጥቅሞላ (አሞና)ጥር 30 ቀን         
23 ጲስጥር 30 ቀን
24 አላጲስ                            ጥር 30 ቀን
25 አጋጲስ                  ጥር 30 ቀን
26 እርሶንያ (አርኒ)           ጥር 30 ቀን
27 ጲላግያጥር 30 እና ጥቅምት 11 ቀን   
28 አንጦልያ (ሉክያ)የካቲት 25 ቀን      
29 አሞን (ሶፍያ)ጥር 15 እና ነሐሴ 3 ቀን         
30 ኢየሉጣነሐሴ 6 ቀን                       
31 መሪናሐምሌ 27 ቀን           
32 ማርታ እኅተ አልዓዛር                                   ጥር 18  እና ግንቦት 27 ቀን 
33 ማርያም የማርቆስ እናትጥር 30 ቀን
34 ሣራ (ሶፍያ) የይሁዳ እናትጥር 30 ቀን    
35 ዮሐና (ዮላና) የኩዛ ሚስትታኅሣሥ 26 ቀን  
36 ሶስናግንቦት 12 ቀን
ምንጭ ነገረ ቅዱሳን

ከቅዱሳት አንስት ምን እንማራለን?

እነዚህ “ቅዱሳት አንስት” በታሪክ ብቻ የሚታወቁ ሰዎች አይደሉም፤ ዛሬም ለእኛ የሕይወት መንገድ የሚያሳዩ መምህራን ናቸው።

📖 እነሱ ጌታን ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ተከትለው ነበር፤ ብዙዎች በፍርሃት ሲሸሹ እነሱ ግን በመስቀል ሥር ቆመው ታማኝነታቸውን አሳዩ።

ይህ የሚያስተምረን —እውነተኛ እምነት በጥሩ ጊዜ ብቻ ሳይሆን፤ በመከራ ጊዜ እንደሚፈተን ያስተምረናል።

📖 እነሱ በፍቅር ተነሥተው ወደ መቃብር ሄዱ፤ “ማን ድንጋዩን ያነሳልናል?” ብለው ወደ ኋላ አልተመለሱም።

ይህ የሚያስተምረን —ፍቅር ፍርሃትን እንደሚያሸንፍ። እግዚአብሔርን በእውነት ከወደድን ምንም ከባድ ነገር እንኳን አያስቆመንም።

📖 እነሱ በትሕትና አገልግለዋል፤ ስማቸው እንዲታወቅ አልፈለጉም። ነገር ግን እግዚአብሔር ከፍ አደረጋቸው፤ የትንሣኤን ዜና በመጀመሪያ ሰሙ ፣ ነጋሪዎችም ሆኑ።

         ይህ የሚያስተምረን —ትሕትና ወደ ክብር እንደሚመራ ያሳያል።

📖 እነሱ በሐዘን ወደ መቃብር ሄዱ፤ በደስታ ተመለሱ።

          ይህም የሚያሳየን —ከመስቀል በኋላ ሁሌ ትንሣኤ እንዳለ ነው።

📖 ሴቶች በቤተክርስቲያን አገልግሎት ያላቸው ሱታፊ እጅግ ትልቅ እንደሆነ ያስገነዝበናል። አምላካችን በደቀ መዛሙርቱ ላይ ወድቆ የነበረው የኃዘንና የተስፋ መቁረጥ ጭጋግ በትንሣኤው ዜና እንዲገለጥ ያደረገው በነዚህ ቅዱሳት አንስት ነው። ይህንን የጌታ አብነት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተቀብላ ዛሬም ቤተ ክርቲያን ለሴቶች ተገቢውን ቦታ ሰጥታ ታከብራቸዋለች፤ እነርሱንም በሚመለከት የአገልግሎት ዘርፍ ታሰማራቸዋለች፤ ከአምላክ እናት ከድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ፤ የአምላክ እናት ከፈጣሪ በታች ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ብላ ስሟን ከፍ በማድረግ ጀምራ፣ ሌሎች በቁጥር የናይወሰኑ በርካታ ሴቶችን በቀኖና ቅዱሳት በማለት ቀንና በአምላክ ቤት ለዘለዓለም የማይጠፋ ስም ሰጥታ ታከብራቸዋለች፤ ስለዚህም በዓለም ላይ ከአሥራ ስድስተኛው ምዕት ዓመት ጀምሮ የተነሳው ፌሚኒስት ንድፈ ሐሳብ፤ (Feminist theory) ቅድስት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንን ሊገዳደር አልቻለም።

በመሆኑም ይህቺን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አብነት አድርጋችሁ ሴቶችን እያሳተፋችሁ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የምታገለግሉ የግቢ ጉባኤ ልጆች የበለጠ አጠንክራችሁ እንድታስቀጥሉት ደግሞ እመክራለሁ።

ስለዚህ እንዳጠቃላይ ክርስቲያኖች የግቢ ጉባኤ ልጆች ሆይ ፦

– በመከራ ጊዜ አንሸሽ።

– በፍቅር እንኖር።

– በትሕትና እናገልግል።

– ተስፋችንን አንተው።

“ክርስቶስ ተነሥቷል!” — “በእውነት ተነሥቷል!” አሜን።

   ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይቆየን!

አዳም

ከመምህር ተስፋ ሚካኤል ታደለ

በቤተክርስቲያን ትውፊት ሐሙስ “የአዳም ሐሙስ” ተብላ የምትታወቀው አዳም የተፈጠረባት ዕለት ስለሆነች ሳይሆን፣ ከገነት ተባርሮ መከራ ሲቀበል እግዚአብሔር የመመለስ ተስፋውን የሰጠበት ዕለት በመሆኗ ነው። (መጽሐፈ አክሲማሮስ ፣ ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ሳዊሮስ ስለ ድኅነተ አዳም በተናገረበት)

አዳም በስድስተኛው ቀን (ዓርብ) ተፈጥሮ በዕለተ ዓርብ ቢበድልም፣ እግዚአብሔር ግን በመከራው ውስጥ ተስፋ እንዲሆነው “በሐሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እምወለተ ወለትከ ወእትቤዘወከ፤ አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንኃለሁ” የሚለውን ቃል ኪዳን በሐሙስ ዕለት አረጋገጠለት። ይህ ዕለት ከአዳም ውድቀት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የድኅነት ብርሃን የታየበት፣ ከፈጣሪው ጋር ዳግም ለመገናኘት ቀጠሮ የተያዘበት ታላቅ የቃል ኪዳን ቀን ነው። (መጽሐፈ አክሲማሮስ ፣ በሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ሳዊሮስ ስለ ድኅነተ አዳም በተናገረበት)

ዕለተ ሐሙስ የአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን (፭ ሺህ ፭ መቶ ዘመን) መጀመሪያ ተደርጋ ትቆጠራለች፤ እግዚአብሔር ለአዳም የገባለት ቃል “አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም አድንኃለሁ ” የሚል ነበር፤ ይህ ቀጠሮ አዳም በስደት ባለበት ወቅት በየሳምንቱ ሐሙስ ሲመጣ ያንን የተስፋ ቃል እንዲያስብና እንዲጸና ረድቶታል።

በሐዲስ ኪዳን አስተምህሮ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳም የገባውን ቃል ኪዳን የፈጸመው በጸሎተ ሐሙስ (በምሥጢር ሐሙስ) ነው። አዳም በዕለተ ዓርብ በበላው ዕፅ ምክንያት ያጣውን የጸጋ ምግብ፣ ጌታችን በሐሙስ ምሽት ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን በመስጠት ካሳ አድርጎለታልና፤ አዳም ሐሙስን በጉጉት ሲጠብቅ እንደነበረ ሁሉ፣ ጌታችንም በዚሁ ዕለት ዝቅ ብሎ እግር በማጠብ የአዳምን ትዕቢት በትሕትና ደመሰሰ። ስለዚህ “የአዳም ሐሙስ” ስንል አዳም ተስፋውን የተቀበለበትንና ክርስቶስ ያንን ተስፋ የፈጸመበትን ምሥጢር በአንድነት የምናስብበት ታላቅ ቀን ማለት ነው። (መጽሐፈ አክሲማሮስ፣ በሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ሳዊሮስ ስለ ድኅነተ አዳም በተናገረበት ምዕ ፪፥፫)

 የአዳም አፈጣጠርና የክብር አክሊል

እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ከመፍጠሩ አስቀድሞ ሰማይንና ምድርን፣ በውስጣቸውም ያሉትን ፍጥረታት ሁሉ አዘጋጅቷል፤ ሊቃውንት ይህንን ሲያብራሩ “ንጉሥ ሳይመጣ አዳራሽ፣ ጌታ ሳይመጣ ግብር አይዘጋጅም” በማለት የሰው ልጅ የፍጥረት ሁሉ ዘውድና ማጠቃለያ መሆኑን ያስረዳሉ።  አዳም የተፈጠረው በስድስተኛው ቀን በዕለተ ዓርብ በሦስት ሰዓት (በሦስተኛው ሰዓት) ሲሆን፣ አፈጣጠሩም ከሌሎች ፍጥረታት የተለየ ነበር። ሌሎች ፍጥረታት በቃለ መለኮት “ይሁኑ” ተብለው ሲፈጠሩ፣ አዳም ግን በሥላሴ ዘንድ “ሰውን በአምሳላችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠር” ተብሎ፣ በእግዚአብሔር እጅ ተበጃጅቶ የተፈጠረ ክቡር ፍጥረት ነው።

አዳም የተፈጠረው ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ (ከውኃ፣ ከእሳት፣ ከነፋስና ከምድር) ነው። እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ከምድር አፈር አበጀው፤ ከዚያም “የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት” (ዘፍ ፪፡፯) በዚህም ምክንያት ሰው ከእንስሳት ተለይቶ የሚያስብ፣ የሚረዳ፣ የሚናገርና በምድር ላይ የእግዚአብሔር ወኪል ሆኖ እንዲኖር ተደረገ። አዳም በአፈጣጠሩ የሥጋና የመንፈስ ውሕደት በመሆኑ፣ ምድራዊውን ዓለም ከመንፈሳዊው ዓለም ጋር የሚያገናኝ ድልድይ ሆኖ ተሾመ። (ሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ምዕራፍ ፷፯)

አዳም በገነት ሲሾም የለበሰው የክብር አክሊልና ልብስ ምድራዊ ሳይሆን መለኮታዊ ብርሃን ነበር፤ በወቅቱ ንጉሥ፣ ካህንና ነቢይ ሆኖ ተሹሞ ነበር፤ ፍጥረታት ሁሉ (አራዊትና አዕዋፍ) ስም እንዲያወጣላቸው ወደ እርሱ መጡ፤ ይህም የእውቀቱና የሥልጣኑ ታላቅነት ማሳያ ነው። መላእክትም እንደ ታላቅ ወንድም ያከብሩት፣ እንደ ሞግዚትም ይንከባከቡት ነበር፤ በገነት ውስጥ ካሉት ዛፎች ሁሉ እንዲመገብ ተፈቅዶለት፤ በደስታና በሰላም እንዲኖር ተደረገ። ይህ የክብር ዘመን አዳም ከፈጣሪው ጋር ፊት ለፊት የሚነጋገርበትና ምንም ዓይነት መከራና ድካም የማያውቅበት የመንፈሳዊነት ጫፍ ነበር።

የአዳም ልዩ የክብር አክሊል “በእግዚአብሔር አምሳል” መፈጠሩ ነው። ይህ አምሳል ማለት ሥጋዊ መልክ ሳይሆን፣ እግዚአብሔር የሰጠው ነፃ ፈቃድ ተጠቅሞ የሚያገኘው በነፍስ በኩል የሚሆንለት ቅድስና ነው ̎ኩኑ ቅዱሳነ እስመ አነሂ ቅዱስ፤ እኔ ቅዱስ ነኛና ቅዱሳን ሁኑ እንዲል፤ ጥበብና ገዥነት ለሰው ልጅ በጸጋ መሰጠቱን ደግሞ በአርኣያ እግዚአብሔር መፈጠሩን ያመለክታል። አዳም በገነት በነበረበት ሰባት ዓመታት፣ ከእግዚአብሔር ጋር በነበረው ኅብረት ምክንያት የሰውነቱ ብርሃን ከፀሐይ ይልቅ ያበራ ነበር፤ ከፍጥረት ሁሉ የላቀና የምድር ሁሉ ጌታ ነበር።

 ፪. ሕገ ገነትና ውድቀት

እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ፈጥሮ በገነት ካኖረው በኋላ፣ በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ፍቅርና ታማኝነትን ይገልጥ ዘንድ የሥነ-ምግባር ሕግን ሰጠው፤ ይኸውም “በገነት ካለው ዛፍ ሁሉ ብላ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ” የሚል ነበር (ዘፍ ፪፥፲፮) ።  ይህቺም ዕፅ በባሕርይዋ ክፉ ሆና ሳይሆን፣ አዳም ፍጡር መሆኑንና ከእርሱ በላይ ፈጣሪ መኖሩን እንዲያውቅ፣ እንዲሁም የታዘዘው በመታዘዝ የሚገኘውን በረከት እንዲረዳ የተሰጠች የፈተና መድረክ ነበረች፤ ይህ ሕግ አዳም ያለውን ነፃ ፈቃድ (Free Will) ተጠቅሞ ለፈጣሪው ያለውን ፍቅር በተግባር የሚያሳይበት መሣሪያ ነበር።

የሰው ልጅ ገነት ውስጥ በታላቅ ክብርና ሰላም መኖሩን የተመለከተው የጽልመት ገዥ ሰይጣን፣ በክፋትና በቅናት ተሞላ። “እንደ እግዚአብሔር ትሆናላችሁ” የሚለውን የሐሰት ተስፋ በመያዝ በእባብ ተመስሎ ወደ ሔዋን ቀረበ። ሰይጣን የተጠቀመበት ስልት እግዚአብሔር የሰጠውን ትእዛዝ እንዲጠራጠሩ ማድረግ ነበርና “በእውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዟልን?” በማለት ጥያቄ በማቅረብ፣ በመቀጠልም “ከእርስዋ በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንዲከፈቱ እንደ እግዚአብሔርም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንድትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው እንጂ አትሞቱም” በማለት የትዕቢትና የጥርጣሬ ዘርን ዘራባቸው።

የአዳምና የሔዋን ውድቀት መነሻው የመብል ፍላጎት ብቻ ሳይሆን፣ “ያለ ፈጣሪ ረዳትነት ራሳችንን ችለን እንደ አምላክ እንሆናለን” የሚል የትዕቢት አስተሳሰብ ነው። ሔዋን የዛፏ ፍሬ ለመብላት ያማረ፣ ለዓይንም የሚስብ መሆኑን ባየች ጊዜ ትእዛዙን በመተላለፍ በላች፤ ለአዳምም ሰጠችው። በዚህም ወቅት የባሕርይ ሞት በላያቸው ላይ ሰለጠነ፤ ሊቃውንት እንደሚገልጹት፣ በዚያች ቅጽበት የለበሱት የብርሃን ልብስ ተገፈፈ፤ ራቁትነታቸውን ሆኑ፤ ይህም ከእግዚአብሔር ጸጋ መለየታቸውን የሚያሳይ መንፈሳዊ ዕራቁትነት ነበር፤ ፍርሃትና ጭንቀትም በልባቸው ውስጥ ተከሰተ፤ ከፈጣሪም ድምፅ መሸሸግ ጀመሩ።

ውድቀቱ በአዳምና በሔዋን ላይ ብቻ ሳይሆን በፍጥረት ሁሉ ላይ ተጽዕኖ አሳደረ፤ እግዚአብሔርም በአዳም ምክንያት ምድር የተረገመች እንድትሆን፣ ለአዳም በወዙ እንዲበላ፣ ሔዋንም እንደዚሁ በምጥና በጭንቅ እንድትወልድ ፈረደባቸው። ከሁሉም በላይ ደግሞ “አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” የሚለው ሥጋዊ ሞትና ከገነት ተለይቶ ወደ መከራ ምድር መሰደድ ትልቁ ቅጣት ነበር። ሆኖም በዚህ ውድቀት ውስጥ እንኳን የእግዚአብሔር ምሕረት አልተለየም፤ አዳም ከገነት ሲወጣ “አድንኃለሁ ” የሚል የተስፋ ቃል ተሰጥቶታል። ይህ ውድቀት ለሰው ልጅ መዳን ምክንያት ለሚሆነው ለዳግማዊ አዳም (ለክርስቶስ) ቤዛነት መሠረት ሆኗል።

፫. ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ የመመለስ ተስፋ

አዳምና ሔዋን ከገነት ሲባረሩ፣ እግዚአብሔር አምላክ ያለ ተስፋ በትኖ አልተዋቸውም፤ አዳም በሠራው በደል ምክንያት በደረሰበት መከራ ተጸጽቶና አዝኖ ባለበት ወቅት፣ እግዚአብሔር “ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንኃለሁ” የሚል ታላቅና የማይታጠፍ የምሕረት ቃል ገባለት፤ ይህ አምስት ቀን ተኩል (፭ ሺህ ፭ መቶ ዘመን) የተባለው ቀጠሮ፣ ለሰው ልጅ የድኅነት ጉዞ መሠረት ሲሆን፤ አዳም ከገነት ሲወጣ በትውልድ መካከል ሲያልፍ ለነበረው ጨለማ እንደ ብርሃን ሆኖ ያገለገለ የተስፋ ስንቅ ነው።

መጽሐፍ ቅዱስ “በእግዚአብሔር ዘንድ አንድ ቀን እንደ ሺህ ዓመት፣ ሺህ ዓመትም እንደ አንድ ቀን ነው” (፪ ጴጥ ፫፥፰) እንዲል፤ አምስቱ ቀናት አምስት ሺህ ዓመታትን ሲወክሉ፣ ግማሹ ቀን ደግሞ አምስት መቶ ዓመታትን ያመለክታል። አዳም በስድስተኛው ቀን (በዕለተ ዓርብ) በስድስት ሰዓት እንደበደለ ሁሉ፣ ጌታችንም በዓርብ ቀን በስድስት ሰዓት በመስቀል ላይ ተሰቅሎ አዳምን ነፃ አውጥቶታል።

አዳም ይህንን ቃል ኪዳን አምኖ በመቀበል፣ በመከራ ምድር በኖረባቸው ዓመታት ሁሉ ዓይኑ ወደ ፈጣሪው ተተክሎ ነበር። አዳም በሲኦል ውስጥ ሆኖ እንኳ ይህንን ተስፋ ይጠባበቅ ነበር።  “አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም አድንኃለሁ” የሚለው ቃል፣ አዳም በሞት ጥላ ውስጥ ሆኖ ለሚጠብቃቸው ልጆቹ ሁሉ ያስተላለፈው የነፃነት ዜና ነው፤ ይህ ተስፋ “የአዳም ሐሙስ” ተብሎ ከሚታሰበው ምሥጢር ጋር የተያያዘ ነው፤ ይኸውም የሰው ልጅ ከመከራ ወደ ደስታ፣ ከስደት(ከግዞት) ወደ ነፃነት ከሲኦል ወደ ገነት የሚመለስበት የተስፋ ቀጠሮ የተቀጠረበት ቀን መሆኑ ነው።

እግዚአብሔር ቃል ኪዳኑን ለመፈጸም በዘመነ ሥጋዌ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ፣ አዳም የጠፋበትን መንገድ ሁሉ ተከትሎ ፈለገው፤ በዕለተ ዓርብም ወደ ሲኦል ወርዶ የአዳምን ነፍስ ሲጠራው፣ አዳም ለ፭ ሺህ ፭ መቶ ዓመታት የጠበቀው ያ በዕለተ ዓርብ የተነገረው ተስፋ ቃል እንደተፈጸመ አስተዋለ፤ ይህም ተስፋ ለአዳም ብቻ ሳይሆን፣ ለሁላችንም የሰው ልጆች የእግዚአብሔር ቃል እንደማይታጠፍና የታመነ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፤ በመሆኑም ዕለተ ሐሙስን ስናስብ፣ አዳም “ወደ ርስቴ ገነት እመለሳለሁ” ብሎ የጠበቀው ያ የተስፋ ብርሃን እውን ሆኖሎት ፣ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመለስ መንገዱ የተከፈተበት የምሥጢር ዕለትነቷን እናከብራለን። (መጽሐፈ አክሲማሮስ ፣ በሃይማኖተ አበው ዘቅዱስ ሳዊሮስ ስለ ድኅነተ አዳም በተናገረበት)

 ፬. የአዳም ኑዛዜና ለልጆቹ ያስተላለፈው “መዝገብ (ንብረት)”

አዳም በዚህ ምድር ላይ የ፱፻፴ (ዘጠኝ መቶ ሠላሳ) ዓመታት ዕድሜውን ካሳለፈ በኋላ፣ የዕረፍቱ ሰዓት መቃረቡን አወቀ። በዚያን ጊዜ ልጆቹንና የልጅ ልጆቹን በአንድነት ጠርቶ እንዲሰበሰቡ አደረገ።  ይህ ጉባኤ ተራ የቤተሰብ ጉባኤ ሳይሆን፣ ለሰው ልጅ ትውልድ ሁሉ የሚተርፍ መንፈሳዊ ኑዛዜ የተላለፈበት ታላቅ ጉባኤ ነበር፤ አዳም በፊታቸው ቆሞ፣ ዓይኖቹ በዕንባ ተሞልተው፣ ስለ ገነት ክብር፣ ስለ ውድቀቱ መራራነትና እግዚአብሔር ስለገባለት የተስፋ ቃል በዝርዝር ነገራቸው።

አዳም ከገነት ሲወጣ በእግዚአብሔር ፈቃድ ይዟቸው የወጣ ሦስት ታላላቅ ንብረቶች ነበሩ፤ እነርሱም ወርቅ፣ ዕጣንና ከርቤ ናቸው፤ እነዚህን ውድ ነገሮች ለልጁ ለሴት (Seth) በአደራ ሲሰጠው፣ እንደ ተራ ንብረት ሳይሆን “መዝገብ” አድርጎ ነበር፤ አዳም በኑዛዜው ላይ እንዲህ አላቸው፦ “እነዚህን ንብረቶች ጠብቁ፤ በመጨረሻው ዘመን ዳግማዊ አዳም (ክርስቶስ) ከድንግል ተወልዶ ሲመጣ ለአምላክነቱ፣ ለክህነቱና ለሞቱ ምልክት ይሆኑ ዘንድ ስጡት።” ይህ መዝገብ ከሴት ወደ ኖኅ፣ ከኖኅ ወደ መልከ ጼዴቅ ሲተላለፍ ቆይቶ፣ በመጨረሻም በሰብአ ሰገል አማካኝነት በቤተልሔም ለተወለደው ለክርስቶስ ቀርቧል። ( THE BOOK OF ADAM AND EVE፤ መጽሐፈ አዳም ወሔዋን፣ አንደኛ መጽሐፍ (Book I) ምዕ. ፴፩ )፣ ሁለተኛ መጽሐፍ (Book II) ምዕ. ፰)

አዳም ለልጆቹ ያስተላለፈው መዝገብ ቁሳዊ ብቻ ሳይሆን፣ ሥነ-ምግባራዊም ነበር። ልጆቹ ከቃየን ልጆች (ከክፉዎች) መንገድ እንዲለዩ፣ ንጽሕናቸውን እንዲጠብቁና እግዚአብሔርን በመፍራት እንዲኖሩ አጥብቆ አዝዟቸዋል፤ ይህ ኑዛዜ አዳም ምንም እንኳ በሥጋ ቢሞትም፣ በተስፋውና በእምነቱ ግን ለልጆቹ ሕያው መሪ ሆኖ መቆየቱን ያሳያል።

አዳም ኑዛዜውን ከፈጸመ በኋላ በዕለተ ዓርብ በዘጠኝ ሰዓት ዐረፈ።  ሊቃውንት አዳም ያረፈበት ሰዓት ጌታችን በመስቀል ላይ ነፍሱን አሳልፎ ለሰው ልጅ ድኅነትን የሰጠበት ሰዓት ጋር አንድ ነው፤ አዳም ሲያርፍ ልጆቹ በመዝገቡና በተስፋው ቃል እየተጽናኑ፣ ፭ ሺህ ፭ መቶ ዘመን እስኪፈጸም ድረስ ያንን የወርቅ፣ ዕጣንና ከርቤ አደራ ሳይለወጥ እንዲቆይ አድርገዋል፤ ይህ የአዳም ኑዛዜ የሰው ልጅ ታሪክ ከመቃብር በላይ በሆነ ተስፋ የታሰረ መሆኑን የሚያሳይ ታላቅ ምስክርነት ነው።

የክርስቶስ ወደ ሲኦል መውረድና አዳምን መጥራት

አዳምና ልጆቹ ለ፭ ሺህ ፭ መቶ ዘመናት በሲኦል ጨለማ ውስጥ ሆነው፣ እግዚአብሔር የገባላቸውን የተስፋ ቃል ይጠባበቁ ነበር፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ካፈሰሰ በኋላ፣ ነፍሱ ከሥጋው ተለይታ ወደ ሲኦል ወረደች፤ ይህ መውረድ በሽንፈት ሳይሆን በድል አድራጊነት ነበር፤ ይኸውም በሲኦል ለነበሩት ነፍሳት ሁሉ የነፃነት አዋጅ የታወጀበትና የሞት ደጆች የተሰበሩበት ታላቅ ምሥጢር ነው፤ ጌታችን ወደ ሲኦል ሲወርድ በብርሃኑ ጨለማውን በትኖታል፤ በዚያም የነበሩት የአዳም ልጆች ሁሉ የጌታን ድምፅ ለመስማት በጉጉት ተጠባበቁ፤ ሐሴትም አደረጉ።

ጌታችን ወደ ሲኦል በወረደ ጊዜ መጀመሪያ የጠራው አባታችን አዳምን ነበር፤ አዳም በበደለ ጊዜ እግዚአብሔር በገነት “አዳም ሆይ ወዴት ነህ?” ብሎ የጠራው ጥሪ፣ በሲኦል ውስጥ “አዳም ሆይ ና ውጣ!” በሚል የመዳን ጥሪ ተተካ፤ ጌታችን አዳምን የጠራው በስሙ ብቻ ሳይሆን፣ እርሱንና የልጅ ልጆቹን ሁሉ ከዲያብሎስ ቀንበር ነፃ ለማውጣት ያለውን ለመዳን የሰጠው የተስፋ ቃል እውን መሆኑን የማመላከት ጉዳይ ነው፤ ይህ ጥሪ ለዘመናት ሲጠበቅ የነበረው የተስፋ ቃል ፍጻሜ ማግኘቱን አበሠረ።

አዳም የጌታን ድምፅ በሰማ ጊዜ መንፈሱ ታላቅ ደስታና ሐሴት ተሞላ፤ ጌታችን ለአዳም የሰጠው ሰላምታ በሲኦል የነበረውን ሐዘንና መከራ ወደ ሰርግና ደስታ ቀየረው። 

ጌታችን ለአዳም “ሰላም ለአንተ ይሁን፤ ዛሬ ከእኔ ጋር ደስ ይበልህ” ሲለው፤ አዳምም አምላኩንና መድኃኒቱን ሲመለከት በፊቱ ተደፍቶ ሰገደ፤ “ጌታዬና አምላኬ ሆይ! ከዚህ ጨለማ ስላወጣኸኝ አመሰግንሃለሁ” በማለት የምስጋና መሥዋዕት አቀረበ፤ ይህ በጌታና በአዳም መካከል የተደረገው የሰላምታ ልውውጥ፣ የሰው ልጅ ከፈጣሪው ጋር ዳግም የታረቀበትና የቀደመው ፍቅር የተመለሰበት ታላቅ ምሥጢር ነው።

ጌታችን አዳምን ከጠራው በኋላ፣ እርሱንም ሆነ በሲኦል ተስፋ አድርገው ይጠባበቁ የነበሩትን ቅዱሳን አባቶችና ነቢያትን ሁሉ ይዞ ወደ ገነት ወጣ። አዳም በአንድ ወቅት በኃጢአቱ ምክንያት የተዘጋችበትን ገነት፣ አሁን በክርስቶስ ቤዛነት ተከፍታ አገኛት። ይህ የክርስቶስ ወደ ሲኦል መውረድና አዳምን መጥራት፣ ሞት ድል የተነሳበትና የሰይጣን ግዛት የፈረሰበት ክስተት ነው።

እኛስ ከዚህ ምን እንማር?

የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች አዳም የተፈጠረበት መንገድ (በእግዚአብሔር እጅ መሠራቱና የሕይወት እስትንፋስ እፍ መባሉ) የሰው ልጅ ምን ያህል ክቡር መሆኑን ያሳያል። ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲ ቆይታችሁ የተለያዩ ̎የአሮጊት ተረት የሚመስሉ̎ ፍልስፍናዎችና ዓለማዊ አመለካከቶች አስተሳሰባችሁን እና አመለካከታችሁን እንዳይበርዘው (፩ ጢሞ. ፬፥፯) ፤ “የእግዚአብሔር አምሳል” እና የፍጥረት ዘውድ መሆናችሁን አስባችሁ ሙት የሆነውን የነዳርዊን የቅዠት አስተሰሰብ ውድቅ አድርጋችሁ ይህ አርኣያና አምሳለ እግዚአብሔርነታችሁን አጠንክራችሁ መያዝ ይኖርባችኋል፤ ይህ ክብር በሥነ-ምግባርና በቅድስና ሊጠበቅ የሚገባው ትልቅ የአደራ ስጦታ ነው፤ ባላጋራችን ሰይጣን በምቀኝነት ቢቀማን መድኃኔዓለም አባታችን እስከ ሞት የሚያደርስ ዋጋ ከፍሎ የመለሰልን ውድ ስጦታችን ነው፤ ጥንተ ጠላታችን ሰይጣን ሥልጣኔ የሚባለውን ጭንብል አድርጎ ዛሬም አምላካችን በመሥዋዕትነት የመለሰልንን ልጅነታችንን ሊቀማን ቋምጦ ይገኛልና “መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።” ስለሆነም ልናውቅበት ይገባናል (ኤፌ. ፮፥፲፪)

በገነት ውስጥ የተቀመጠችው አንዲት ዛፍ ለአዳም የነፃነቱና የታማኝነቱ መለኪያ ነበረች፤ በተመሳሳይ መልኩ፣ በግቢ ቆይታ ውስጥ የሚገጥሟችሁ ልዩ ልዩ ፈተናዎች የእናንተን መንፈሳዊ ጥንካሬን የሚፈትኑ ናቸው። አዳም በትዕቢትና በጥርጣሬ እንደወደቀው ሳይሆን፣ ተማሪዎች ̎የዓይን አምሮት የሥጋ ምኞት̎ ሳይበግራችሁ የቤተክርስቲያንን ሕግና ሥርዓት ጋሻ መከታ አድርጋችሁ፣ ̎የእግዚአብሔር ዕቃ ጦር አንስታችሁ̎ ለአምላካችን ያላችሁን ፍቅር በታማኝነት በተግባር ልትገልጡ ይገባል። (ኤፌ. ፮፥፲፫)

አዳም ከገነት ቢወጣም፣ንስሓ መግባቱና ለ፭ ሺህ ፭ መቶ ዘመን በተስፋ መጠባበቁ በትንሽ ነገር ተስፋ ለምንቆርጠው ለእኛ ትልቅ ትምህርት ነው፤ የሰው ልጅ ደካማ ነውና በሐሳብም ሆነ በተግባር ሊወድቅ ይችላል፤ ዋናው ቁም ነገር ግን በውድቀት ውስጥ አለመቅረት ነው። “አድንኃለሁ” የሚለው መለኮታዊ ቃል ኪዳን ዛሬም በንስሓ ለሚመለሱ ሁሉ ክፍት ነው፤ ስለሆነም ተማሪዎች በሕይወታችሁ ስሕተት ብትሰሩ እንኳ እንደ አዳም ወደ ፈጣሪያችን በመጮህና የእርሱ ወደር የሌለው ምሕረት ተስፋ በማድረግ መነሳት እንዳለባችሁ ነው የሚያስገነዝበው።

አዳም ለልጆቹ ያስተላለፈው “የመዝገብ አደራ” (ወርቅ፣ ዕጣንና ከርቤ) ለዘመናት ተጠብቆ ለክርስቶስ መቅረቡ፣ በትውልድ መካከል ያለውን መንፈሳዊ ሰንሰለት ያሳያል፤ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ከቤተሰቦቻቸውና ከአባቶቻቸው የተቀበሉትን ሃይማኖታዊ ዕሴትና ሥነ-ምግባር ሳይበረዝ ለሚቀጥለው ትውልድ የማስተላለፍ ኃላፊነት አለባቸው፤ ሃይማኖታችን ወደእኛ የደረሰችውም በትውፊት ነውና፣ የግቢ ጉባኤ አገልግሎት ለቀጣይ ትውልድ ተሻጋሪ እንዲሆን ጠንክሮ በመሥራት ኃላፊነትን የሚሸከም ትውልድ ማፍራት ላይ መሥራትና ለኃላፊነት ብቁና ዝግጁ እንዲሆን ለተተኪው ሊወጡት የሚችሉትን ተግባር መስጠት ያስፈልጋል፤ በዕውቀት ብቻ ሳይሆን ለአደራ ያላቸው ታማኝነትም ሊታወቅ ይገባል።

ጌታችን ወደ ሲኦል ወርዶ አዳምን “ዛሬ ከእኔ ጋር ደስ ይበልህ” ብሎ መጥራቱ የመጨረሻው የፍቅር ጥግ ነው፤ እንደዚሁ ተማሪዎች በግቢ ቆይታቸው እርስ በርስ በሚኖራቸው መስተጋብር የክርስቶስን ትሕትና ሊላበሱ ይገባል፤ ይኸውም የወደቁትን በማንሳት፣ የተቸገሩትን በመርዳትና በይቅርታ በመኖር የአዳም ልጆች መሆናቸውን ሊያስመሰክሩ ይገባል። ድኅነት የተገኘው በትሕትና እንደሆነ ሁሉ፣ ስኬትም የሚገኘው በትሕትና መሆኑን ማስተዋል ያስፈልጋል። 

ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይቆየን!

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን

ከመምህር አበበ ፍቅሬ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን

ከበዓለ ትንሣኤ በኋላ ያሉ የሳምንታቱ ዕለታት የራሳቸው ስያሜ ተሰጥቷቸዋል። ከእነዚህ ዕለታት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ዕለተ ዓርብን ቤተ ክርስቲያን በማለት ሰይመዋታል። ዓርብ የሚለው ዐረበ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ተካተተ የሚል ትርጕም አለው። ይህም የፍጥረት መካተቻ ቀን መሆኑን የሚያመልክት ነው።

ይህች ዕለት እግዚአብሔር ̎ሰውን በአርኣያችንና በአምሳያችን እንፍጠር ብሎ አዳምን የፈጠረባት ናት፤ (ዘፍ. ፩፥፳፮) በእግዚአብሔር አርኣያና አምሳል የተፈጠረው አዳም ይህንን አምሳለ እግዚአብሔርነቱን በበደሉ ምክንያት ሲያጣ አካላዊ ቃል በተለየ አካሉ ሰው ሆኖ በሐዲስ ተፈጥሮ ወደ ቀደመ ቦታው የመለሰባት ዕለት መሆኗን ሊያጠይቁ ዕለቲቱን ቤተ ክርስቲያን ብለው ሰይመዋታል።

በሊቃውንት ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ሲባል ሦስት ዓይነት ትርጕም ተሰጥቶት እናገኛለን፤ የመጀመሪያው የክርስቲያን ሰውነት ቤተ ክርስቲያን ይባላል፤ ሁለተኛው የክርስቲያን ኅብረት አንድነት ሲሆን ሦስተኛው ደግሞ አምልኮ የሚፈጸምበት ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ይሰኛሉ።

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን

ቤተ ክርስቲያን የሚለው ስያሜ ቤትና ክርስቲያን ከሚሉት የቃላት ጥምርታ የተገኘ ሲሆን፣ ቤተ አደረ፣ ክርስቲያን ከግሪክና ላቲን ቃል ተገኝቶ ክርስቶሳዊ የሚል ትርጕም ሲኖረው፣ አንድ ላይ የክርስቲያኖች ማደሪያ፣ መጸለያ የሚል ይሆናል።

በዘመነ ብሉይ በተለያዩ ስያሜያት ሲጠራ እናስተውላለን፤

ቤቴል ይባላል።

 ̎ለሐውልት የተከልሁት ይህም ድንጋይ የእግዚአብሔር ቤት ይሆናል (ዘፍ. ፳፰፥፳፪) ያዕቆብ ድንጋይ አቁሞ የሜሮን ምሳሌ የሆነውን ዘይት ያፈሰሰበት ቦታ ነው።

ቤቴል ማለት ቤተ እግዚአብሔር ማለት ነው። እንደሚታወቀው ትውልድ ከአምልኮተ እግዚአብሔር ለዓይን ጥቅሻ ያህል ፈቀቅ ባይልም የአምልኮ ቤተ መቅደስ ግን የተሠራው 1100 ቅ.ል.ክ (ቅድመ ልደተ ክርስቶስ) በንጉሥ ሰሎሞን ነው፤ ከዚያ በፊት የነበረው የመገናኛ ድንኳን ሲሆን ንጉሥ ዳዊት ለመሥራት ዕቅድ በያዘ ጊዜ እግዚአብሔር ̎…ልጅህ እርሱ ለስሜ ቤት ይሠራል እንጂ ቤት የምትሠራልኝ አንተ አይደለህም (፩ኛነገ. ፰፥፲፱) ብሎ ̎የምትሠሩልኝ ቤት ምን ዓይነት ነው? የማርፍበትስ ስፍራ ምንድር ነው?̎ ብሎ እንደጠየቀ (ኢሳ.፷፮፥፩) ምንም እንኳ በቦታ የማይወሰን በሁሉ የመላ ቢሆንም በኵነት ያይደለ በረድኤት ሊያድርበት ለጠቢቡ ሰሎሞን እንዲሠራለት የፈቀደለት ይህ የእግዚአብሔር ቤት ይባላል።

̎ነሐውር ቤተ እግዚአብሔር በአሐዱ ልብ፤ በአንድ ልብ ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ፤ (መዝ. ፶፬፥፲፬) ፤ ̎ተፈሣሕኩ እስመ ይቤሉኒ ቤተ እግዚአብሔር ነሐውር፤ ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ (መዝ. ፻፳፩፥፩) በማለት እንደተናገረ ነቢዩ ዳዊት።

ቤተ ጸሎት ይባላል።

 ̎ወደ ተቀደሰ ተራራዬ አመጣቸዋለሁ፥ በጸሎቴም ቤት ደስ አሰኛቸዋለሁ፤ ቤቴ ለአሕዛብ ሁሉ የሚሆን የጸሎት ቤት ይባላልና የሚቃጠለውን መሥዋዕታቸውንና ሌላ መሥዋዕታቸውን በመሠዊያዬ ላይ እቀበላለሁ።” (ኢሳ. ፶፮፥፯) ፣ (ማቴ. ፳፩፥፲፫)

አማኞች ጸሎት የሚጸልዩበት፣ መሥዋዕት የሚሠዉበት፣ በአጠቃላይ መንፈሳዊ ተግባራት በሙሉ የሚከውኑበትና ለእነዚህ ተግባራት መከወኛ የሚሆኑ ንዋያተ ቅድሳት የሚገኝባት፣ የሰው ልጅም የሚቀደስባት መካነ ዕረፍት (የዕረፍት ቦታ) ሆና የሥጋና የነፍስ ዕረፍት የምትሰጥ ስለሆነች አምላካችን በዚህች ቦታ መኖር እንደሚገባን ሲነግረን ̎በአባቴ ቤት እሆን ዘንድ እንዲገባኝ አላወቃችሁምን?̎ ሲል መጠየቁን ልብ ይሏል።(ሉቃ. ፪፥፵፱)

በዕለተ ዓርብ አምላካችን ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ መሥዋዕት አቅራቢ፣ ራሱ መሥዋዕት ተቀባይ ሆኖ ድኅነተ ሥጋ እንጂ ድኅነተ ነፍስ በማያስገኘው በኦሪት መሥዋዕትና ክህነት ምትክ መሥዋዕቱ ከነሙሉ መሠዊያውና ሥርዓተ መሥዋዕት ቀይሮ ቤተ ክርስቲያን በትክክል የገነት (መንግሥተ ሰማይ) ምሳሌ መሆኗን ያረጋገጠባት ታላቅ ዕለት ናት።

የምእመናን ኅብረት(አንድነት)

የምእመናን ኅብረት ቤተ ክርስቲያን በመባል ትጠራለች። ይህም ኤክሌሲያ ከሚለው የግሪክ ቃል የተገኘ ሲሆን ኀሪት (የተመረጠች)፣ ጽውዕት (የተጠራች) ጉባኤ የሚል ትርጕም የያዘ መሆኑን ሊቃውንቱ ያብራራሉ፤ ሽማግሌዎች በጎ ሥራ የሚሠሩበትንም ጉባኤ ስሙ ኤክሌሲያ በማለት ግሪኮች እንደሚጠቀሙበት ይታወሳል፤ መመረጥና መጠራት የሚለው ሙሴ ሕዝበ እግዚአብሔርን እንዲያስተዳድሩ ሰባ ሊቃናት በኢትዮጵያዊው አማቹ ዮቶር ምክር ተነሥቶ የመረጣቸውን ተያይዞ እስከወዲያኛው የዘለቀ ሥርዓት ሆኖ ሥርዓት ሲሠሩ፣ ሕግ ሲያወጡ ሲያስፈጽሙ እስራኤልን ያስተዳድሩ የነበሩትን ሲያዘክር ነው።

ወጥ የሆነ ሕግ፣ ሥርዓት፣ ትውፊት፣ ቀኖና፣ እምነት ያለን በክርስቶስ ኢየሱስ ዳኝነት በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር የምንሰበሰብ ̎አንድ ልብ ያለን፣ ̎ራሳችን ክርስቶስ እኛ አካሉ የሆንበት፣ ምግባችን ሥጋ መለኮት፣ መጠጣችን ደመ መለኮት የሆነበት፣ ከአምስቱ የስሜት ሕዋሳት መጥቀን በስድስተኛው የስሜት ሕዋስ በመንፈስ የምንግባባበት፣ ̎በአንድ ልብ አስበን በአንድ አፍ ተናግረን አንድ ውሳኔ የምንወስንበት ጉባኤ የምእመናን ኅብረት ኤክሌሲያ ቤተ ክርስቲያን ናት፤

ብሉይ ኪዳን ለሐዲስ ኪዳን ጥላ፣ አምሳል፣ መርገፍ፣ መስታወት እንደመሆኑ፣ ኤክሌሲያም ለቤተ ክርስቲያን እንዲሁ ነው፤ ምክንያቱም ምድራውያን ብቻ ሳይሆኑ፣ ምድራውያኑ ከሰማያውያን ጋር ኅብረት የፈጠሩበት መሆኑን በክርስቶስ ልደት “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ስምረቱ ለሰብእ፤ ምስጋና ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን፣ ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ…” (ሉቃ. ፪፥፲፬) አሉ ምድራውያንም ከመላእክቱ በጋራ ዘመሩ፤ በዚህም አንድነት ተወጠነ፤ በደብረ ታቦርም በብሔረ ሕያዋን ያለው ኤልያስ፣ በብሔረ ሙታን ያለው ሙሴና በምድር የሚገኙት ሦስቱ የምሥጢር ሐዋርያት የተባሉት ያዕቆብ፣ ዮሐንስና ጴጥሮስ ተገኝተው በአጸደ ነፍስና በአጸደ ሥጋ የሚገኙ የአዳም ልጆች ኅብረት እንደሆነች ታወቀች፤ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያን ኲላዊት ትባላለች፤ በምድር፣ በሰማይ፣ በሀገር በአህጉር፣ በቋንቋ፣ በነገድ የማትከፈልና “የሁሉ ፤ Universal” በመሆኗ ነው።

ሰዎች በባሕርዩ ቅዱስ የሆነ አምላክን ለማምለክ በስሙ የተጠሩ፣ በስሙ ቅዱስ ተግባር እየፈጸሙ “ኲኑ ቅዱሳነ እስመ አነሂ ቅዱስ፤ እኔ ቅዱስ ነኛና ቅዱሳን ሁኑ” እንዲል ፍለጋውን በመከተል ቅድስና ገንዘብ የሚያደርጉባት መንገድ በመሆኗም “ቅድስት፤ Holy” ትባላለች።

“ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ አንዲትም ነፍስ ነበሩአቸው፥ ገንዘባቸውም ሁሉ በአንድነት ነበረ እንጂ ካለው አንድ ነገር ስንኳ የራሱ እንደ ሆነ ማንም አልተናገረም።” (ሐዋ. ፬፥፴፪) እንዲል፣ እነ እገሌ የመሠረቷት የእነ እገሌ ቤተ ክርስቲያን የለችም፤ በአንድ በክርስቶስ ደም ተመሥርታለች እንጂ፣ ̎እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ፤ ገበሬውም አባቴ ነው። ፍሬ የማያፈራውን በእኔ ያለውን ቅርንጫፍ ሁሉ ያስወግደዋል፤ (ዮሐ. ፲፭፥፩-፪)

̎አካልም አንድ እንደ ሆነ ብዙም ብልቶች እንዳሉበት ነገር ግን የአካል ብልቶች ሁሉ ብዙዎች ሳሉ አንድ አካል እንደ ሆኑ፥ ክርስቶስ ደግሞ እንዲሁ ነው፤ አይሁድ ብንሆን የግሪክ ሰዎችም ብንሆን ባሪያዎችም ብንሆን ጨዋዎችም ብንሆን እኛ ሁላችን በአንድ መንፈስ አንድ አካል እንድንሆን ተጠምቀናልና። ሁላችንም አንዱን መንፈስ ጠጥተናል። (፩ኛቆሮ. ፲፪፥፲፪-፲፫)

ይህ በጠቅላላ የገለጥነው ስለ ተጋዳይዋ ቤተ ክርስቲያን (Church Militant) ነው፤ ስለ ድል አድራጊዋ ቤተ ክርስቲያን (Triumphant church) ከተባለችው ከትንሣኤ ዘጉባኤ በኋላ ስላለችው ስንናገር ደግሞ ከዚህ እጅግ የጠነከረ ይሆናል፤ ማለትም ምእመናን የተፈጠሩበት ተግባር ወደ ሆነው ወደ እግዚአብሔር ምስጋና ያለምንም የሐሳብ መከፈል በፍጹም ልብ ይጠቃለላሉና፤ ምክንያቱም ሌላ ምንም የሚያሳስባቸው ሥጋዊ አስተሳሰብ በዚያ አይኖርም።

ይህ የምእመናን አንድነት መተሳሰብና መደጋገፍ ያለበት ፍቅረ ቢጽ የሚገለጥበት እንደመሆኑ አምላክ የሚወደው እንደሆነ ልበ አምላክ ዳዊት ̎ናሁ አዳም ወናሁ ሠናይ ሶበ ይሄልው አኃው ኅቡረ፤ ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ እነሆ መልካም ነው፣ እነሆም ያማረ ነው።” (መዝ. ፻፴፫፥፩) ብሎ ሲገልጠው፤ አምላካችንም ̎እንዘ ግቡአን በስምየ ክልኤተ ወሠለስተ አነ እሄሉ ማእከሌሆሙ ህየ፤ ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና።” (ማቴ ፲፰፥፳) ብሎ የነቢዩን ቃል አጠነከረው፤ ጽኑእነቷንም ሲያስረዳ ̎ለቤተ ክርስቲያን ንገራት አለ። (ማቴ. ፲፰፥፲፯)

“እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ፤” (፩ኛ ጴጥሮስ ፪፥፱) ካሌዎካሌ የሚለውን የጽርዕ ቃል ፍቺው እዚህ ጋር ይገኛል።

“ለእግዚአብሔር ቤተ መቅደስም ከጣዖት ጋር ምን መጋጠም አለው? እኛ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነንና እንዲሁም እግዚአብሔር ተናገረ እንዲህ ሲል፦ በእነርሱ እኖራለሁ በመካከላቸውም እመላለሳለሁ፥ አምላካቸውም እሆናለሁ እነርሱም ሕዝቤ ይሆናሉ።” (፪ኛ ቆሮ. ፮፥፲፮) እያለ ደግሞ ምንም እንኳ ከጨለማ ለይቶ ወደ ሚደነቅ ብርሀን በብርሀኑ ቢጠራንም ያ ለይቶ ከጠራን ጨለማ ከተሰኘ ከጣዖት ጋር ኅብረት እንዳይኖረን ያስረዳናል።

የአማኝ ሰውነት

የሥላሴ ልጅነት ያገኘ ክርስቲያን ሰውነቱ ቤተ ክርስቲያን ተብሎ ይጠራል፤ ቤተ ክርስቲያን ማለት ማኀደረ እግዚአብሔር የሚል ትርጕም አለውና፤ ማደርያነቱም በድንግል ማርያም ሲያድር ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ በኵነት ሲሆን፤ በጥምቀት ልጆች በሆኑ በአማኒ ያን ያደረው ደግሞ በረድኤት ነው፤ “እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ፤ ማንም ድምፄን ቢሰማ ደጁንም ቢከፍትልኝ፥ ወደ እርሱ እገባለሁ ከእርሱም ጋር እራት እበላለሁ፤ እርሱም ከእኔ ጋር ይበላል።” (ራእ. ፫፥፳) “ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል እኔም በእርሱ እኖራለሁ።” (ዮሐ. ፮፥፶፮) እንዲል እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ሰውነታችን ከኃጢአት ለይተን በቅድስና ለአምላካችን ስንሰጠው ሱታፌ አምላክ በመቀበል ከአምላካችን ጋር የምንሆንበት ነው።

በእግዚአብሔር አምሳልና አርኣያ የተፈጠረ፣ በበደል ምክንያት ቢተዳደፍ በማየ ገቦ፣ በጥምቀት ልጅነት አግኝቶ በቅብዐ ሜሮን ከብሮ በእግዚአብሔር ልጅ ሥጋና ደም ታድሶ ወደ ቀደመ ክብሩ የተመለሰው ይህ የሰው አካል የእግዚአብሔር ሕግጋትን ሲተላለፍ ደግሞ የእግዚአብሔር ማደሪያ ከመሆን ይፈርስና የርኵስ መንፈስ ማደርያ ይሆናል። (፩ኛ ቆሮ. ፫፥፲፮-፲፯፤ ፮፥፲፱-፳)

አሁን በተጨባጭ ያሉብን ተግዳሮቶችና መፍትሔዎቻቸው

በግል ሕይወታችን

ዘመኑ ድኅረ ድኅረ ዘመናዊነት፤ (post post modernism) እንደመሆኑ መጠን ቴክኖሎጂው በየቀኑ የሚፈጥራቸው፤ ቁሶችና ሐሳቦች ተፈጥሮን የሚገዳደሩ፤ ስብእናን የሚጻረሩ፣ አምላክን የመያሳዝኑ፣ ትውልዱም ከባህል፣ ከሥርዓት፣ ከሞራል፣ ከሃይማኖትና ከመሳሰሉት ጠንካራ ዕሴቶች የሚነጥሉ ናቸው።

ማምለጫ መንገድ (መፍትሔ)

፩. ዘመኑን በሚገባ መዋጀት፡- “ዘመኑን እየዋጃችሁ፥ በውጭ ባሉቱ ዘንድ በጥበብ ተመላለሱ።” (ቆላ. ፬፥፭) ፤ እንግዲህ እንደ ጥበበኞች እንጂ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንዴት እንድትመላለሱ በጥንቃቄ ተጠበቁ፤ ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና ዘመኑን ዋጁ። (ኤፌ. ፭፥፲፭) ይህህ ማለት ለሚመጡ የቴክኖሎጂ ግኝቶች ሁሉ እንደ እንግዳ ነገር ቆጥረነው ግር መሰኘት አያስፈልግም፤ የሚጠቅም ከሆነ ቶሎ መላመድ የማይጠቅም ከሆነ ማስወገድ ይገባል፤ ሌላው አጠቃቀሙን በተገቢው መንገድ ማድረግ፤ ይህ ሲባል አንድ ግኝት በጎ እንዲሁም ጎጂ ጎን ይኖረዋልና ነው። ይህ ካልሆነ ጎጂ ጎኑን ብቻ ዓይተን የምናስወግደው ከሆነ ከዘመኑ ጋር አብሮ መላመድ አይቻልምና፤ መርዙን አስወጥቶ ብልሀቱን መጠቀም ይገባል።

ከአሉባልታ ወሬ መታቀብ፡- እስከነ ብሂሉ ̎ወሬ የለውም ፍሬ አበባ የለውም ገለባ ነውና ያለአመክንዮ በግብታዊነት የሚናገሩ አሳች ሰዎችን መስማት ሳይሆን ትክክለኛ መረጃን መያዝ ይገባል።

፫. በዓለት ላይ መመሥረት፡- ይህም ዓለት የተሰኘው ቃለ እግዚአብሔርን በሚገባ መማር ከአሉባልታ ለይቶ ትክክለኛ አካሄድን ያመላክተናል፤ “ሕግህ ለእግሬ መብራት፥ ለመንገዴ ብርሃን ነው።” (መዝ. ፻፲፱፥፻፭) ስለሆነም በሆነው ባልሆነውም ነገር ሳንሸበር በርጋታ እንኖራለን፤ ̎ዐላዋቂዎችን ከጥበብ መራቅ ይገድላቸዋልና፥ ሰነፎችንም ቸልተኛ መሆን ያጠፋቸዋልና። የሚሰማኝ ግን በርጋታ ይቀመጣል፥ ከመከራም ሥጋት ያርፋል። (ምሳሌ ፩፥፴፪-፴፫) እንዲህ ከሆነ በነገሮች መደናገጥ ሳይሆን ንስሓ መግባት፣ መቍረብ በጎ ምግባራትን መሥራትን እናዘውትራለን። ካልሆነ ደግሞ ወደነፈሰው እንነፍሳለን፤ ሽብርና ወከባ እየናደን በአሸዋ ላይ እንደተመሠረተ ቤት እንፈርሳለን። በተለይ የጌቢ ጉባኤ ተማሪዎች እናንተ ከዕድሜ አኳያ፤ ከትምህርቱ ጋር ተያይዞ ውስጣዊና ውጯዊ ፈተናዎች በላያችሁ ስለሚያንዣብቡ አጠንክራችሁ የግቢ ጉባኤ መርሐ ግብራትን መከታተልና በአገልግሎት መጽናት ይኖርባችኋል።

የምእመናን አንድነት

ነገደ እስራኤል (ሕዝብና አሕዛብ) ከሚለው የብሉይ የአምልኮ ሥርዓት በክርስቶስ ደም ተዋጅታ የተመሠረተችው ቅድስት፣ ኵላዊት፣ አሐቲ፣ ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን የታሪክ ምሁራን እንደሚገልጹት በተለያየ ዘመን በዓለም ላይ መከፋፈል እንደተፈጠረ እሙን ነው፤ ለዚህም ዋነኛ መንሥኤ የምንፍቅና ጉዳይ እንዳለ ሆኖ የሥልጣን በላይነት የማንጸባረቅ ጉዳይ መሆኑ ነው፤ ዛሬም የዘርና የፖለቲካ ጉዳይ ቤተ ክርስቲያንን እንዴት እንደሚያውካት ተረድተን ልንታገልና ከሥጋ ማንነታችን ይልቅ ለሰማያዊ ዜግነታችንን ቅድሚያ ሰጥተን በክርስቶስ የሆነው ኅብረታችን ልንጠብቅ ያስፈልጋል።

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን

እነዚህ ከላይ የተመለከትናቸው ሁለቱን ጉዳዮች በአግባቡ ከጠበቅን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያናችን ጠብቀናትል ማለት ነው፤ የክርስቶስ አካል የሆነ አማኝ ከነጻ ኅብረታችን በዘረኝነት ካልተበከለ አምላካችን ̎ዝየ አኀድር፤ በዚህ አድራለሁ ይላል፤ ካልሆነ ግን ለግፈኞች አሳልፎ ይሰጣታል።

ስለዚህ በበጎ ምግባራት በመጸናት፣ ራሳችን በንስሐ በማንጻት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ልንኖር ይገባል።

ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር!

ቶማስ

መምህር ተፈሪ መንገሻ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከትንሣኤ ጀምሮ ያሉትን ዕለታት ትርጉም ባለው ምሥጢር በመሰየም ከትንሣኤው ጋር እያገናኘች ልጆቿን በምሥጢር ሰረገላ ራስ ወደ ሆናት ክርስቶስ ታሳርጋቸዋለች።

ዕለተ ማክሰኞም “ቶማስ” ትባላለች።

ለምን ተሰየመ? ምሥጢሩና አሁን ላለው ዓለም የሚያንጸባርቀው ታላቅ እውነት ምንድነው? እንመለከተዋለን።

ቶማስ ማለት ፀሐይ ማለት ነው። ጌታችን ለመግደላዊት ማርያም ከተገለጠላት በኋላ ጌታ በተነሣባት ዕለት ምሽት ላይ ሐዋርያት አይሁድን በመፍራት ደጃቸውን ዘግተው በቤት ውስጥ ተቀምጠው ነበር። ጌታችንም መዝጊያን ሳይከፍትለት በመካከላቸው ተገኝቶ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው።

በዚህም ጌታችን ደቀመዛሙርቱ መምህራቸው ይመራቸውና ሁሉን ጥለው የተከተሉት ጌታ በሮማውያን ጭፍሮች ተይዞ፣ ተሰቅሎ ሞቶ ባለበት ሰዓትና እኛንም ይገድሉናል በሚል ታላቅ ፍርሀት ውስጥ ባሉበት ሰዓት በርግጥም “ሰላም” ያስፈልጋቸው ነበር።

እንዲሁም ደጆች ተዘግተው ባሉበትና እያንዳንዷ ኮሽታ በሚያስደነግጣቸው ሰዓት በር ሳይከፈት በመካከላቸው ተገኝቶ መቆሙ ከምንም በላይ ያልጠበቁትና የሚያስደነግጣቸው ነውና በቅድሚያ ውስጣቸው ሊረጋጋ ያስፈልጋልና “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው። “ይህንም ብሎ እጆቹንም ጎኑንም አሳያቸው። ደቀ መዛሙርቱም ጌታን ባዩ ጊዜ ደስ አላቸው።” ዮሐንስ ፳፥፲፱-፳።

ይህም የሥጋና የመለኮት ተዋሕዶ ከትንሣኤ በኋላም አንድ እንደሆነ ያሳያል። ግዙፉ ሥጋ የመለኮትን ረቂቅነት ረቂቁ መለኮት ደግሞ የሥጋን ግዙፍነት ገንዘብ ማድረጉን የሚገልጽ ድንቅ ምሥጢር ነው። እንዲሁም በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፬ ላይ እንደተገለጸው ለሐዋርያት በተገለጸላቸው ጊዜ “ነገር ግን ደነገጡና ፈሩ መንፈስም ያዩ መሰላቸው” ስለሚል

አሁን በፊት ለፊታቸው የሚመለከቱት ሥጋ ከሦስት ቀን በፊት በመስቀል ላይ ያንን ሁሉ መከራ የተቀበለውና የሞተው መሆኑን ለመግለጽ ነበርና “እኔ ራሴ እንደሆንሁ እጆቼንና እግሮቼን እዩ፤ በእኔ እንደምታዩት፥ መንፈስ [ምትሀት] ሥጋና አጥንት የለውምና እኔን ዳስሳችሁ እዩ አላቸው።”

አንድም እንደነ ቅዱስ ቄርሎስና ቅዱስ ኤፍሬም እንዲሁም አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እንደተረጎሙት የጌታን በዝግ ቤት መግባቱንና ከኅቱም መቃብር መውጣቱን ከኅቱም ድንግልና መወለዱ ጋር በማገናኘት ሰውም አምላክም መሆኑን የገለጸበት መሆኑን ይናገራሉ።

በዚህም ጌታችን አምላክ እንደመሆኑ በዝግ ቤት ሲገባ ሰው እንደመሆኑ ደግሞ የተወጋውን እጆቹንና ጎኑን በማሳየት ያ አንዱ ሥግው ቃል ከትንሣኤ በፊትና በኋላም በተዋሕዶ የጸና መሆኑን ልብ ይሏል።

ነገር ግን ቶማስ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል በዚያ ቤት አልነበረም። በኋላም ጌታን እንዳዩት በነገሩት ጊዜ ትንሣኤውን በቀላሉ ማመን አልፈለገም። “የችንካሩን ምልክት በእጆቹ ካላየሁ ጣቴንም በችንካሩ ምልክት ካላገባሁ እጄንም በጎኑ ካላገባሁ አላምንም አላቸው።” (ዮሐ. ፳፥፳፭) ቶማስ ሌሎቹ ደቀ መዛሙርት አየነው ስላሉት “ካላየሁ አላምንም” ብቻ ሳይሆን ከማየትም አልፎ “ካልነካሁ አላምንም” የሚል ጭምር ነበር።

የቶማስ ጥርጣሬ ከክህደት የመነጨ የልብ መደንደን አልነበረም፤ ይልቁንም ጌታችን ለዓለም ሁሉ የትንሣኤውን እውነት የሚያትምበት መሣሪያ እንጂ። ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “የቶማስ አለማመን ከሌሎቹ ሐዋርያት ማመን ይልቅ እምነታችንን አጸናው” በማለት እንደተረጎመው፣ ቶማስ በኛ ቦታ ሆኖ ጠየቀ፤ በኛ ቦታ ሆኖ መረመረ፤ የእርሱ መጠራጠር እኛ እንድናምን አደረገ።

ከትንሣኤው በኋላ ያለው የክርስቶስ አካል ያ በመስቀል ላይ የዋለው፣ የተቸነከረውና የተወጋው ትክክለኛው ሥጋ መሆኑን (የተዋሕዶን ምሥጢር) ለማረጋገጥ ነበር።

ጌታችን ለሌሎች ተገልጦ ለቶማስ ለስምንት ቀናት ሳይገለጥለት ቆየ። ይህ ሁሉ ምክንያት ነበረው ሌሎች ሐዋርያት ጌታን ስላዩት ሲፈነድቁ ቶማስ ግን ይህንን በመሰለ ጥርጣሬ ውስጥ እያለ ወዲያው አለመገለጡ ውስጡ ላይ ይህንን እውነት የማየት ፍላጎቱ እንደ ማዕበል እንዲቀሰቀስ፣ የናፍቆት እሳቱም ይበልጥ እንዲፋፋም አደረገው።

እኛም በሕይወታችን ውስጥ የምንፈልገው ነገር ወዲያው ሳይሳካ ቀርቶ ሲዘገይ፣ ውስጣዊ ፍላጎታችን እንደ ማዕበል መናወጡ ለጸሎትና ለተጋድሎ ብርታትን የሚሰጥ መንፈሳዊ ጥማት እንዲኖረን ያደርጋል።

ይህም መዘግየት ልክ እንደ ቶማስ ስምንት ቀናት ሁሉ፣ እምነታችን ከመስማት አልፎ ወደ ጥልቅ እርግጠኝነት እንዲሸጋገር የሚረዳ ሲሆን፣ መጽሐፍ ቅዱስም ይህንኑ ሲያጸና “ነፍሴ እግዚአብሔርን ትጠማለች፤ በውኑ መቼ እደርሳለሁ? የአምላክንስ ፊት መቼ አየዋለሁ?” (መዝሙር ፵፩፥፪) በማለት የመሻታችንን ፋና ይበልጥ ያበራዋል።

የጌታችንን የፍቅሩን ጥልቀትና የትሕትናውን ስፋት እስኪ በአንክሮ ተመልከቱ! የሰውን ልጅ ከተጠማበት የኃጢአት ድርቀት ሊያረካ በቀትር ፀሐይ ለአንዲት ሳምራዊት ሴት ሲል በውኃ ጉድጓድ አጠገብ የጠበቀው ያ የነፍሳት ታላቅ እረኛ፤ አሁንም ለአንዲት ለምትጠራጠር ነፍስ ሲል በዝግ በር ውስጥ አልፎ ገባ። ዐሥሩ ደቀ መዛሙርት በቦታው ነበሩ፤ የጌታችን ዐይኖች ግን የፈለጉት አንዱን ቶማስን ብቻ ነበር። ቀጥታ ወደ እርሱ ሄደ፤ ቶማስንም አነጋገረው።

“ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን አለው።” ዮሐንስ ፳፥፳፯

ቶማስ “የችንካሩን ምልክት ካላየሁ…” ብሎ የተናገረው ለብቻው ሆኖ አልነበረም፤ ሌሎች ሐዋርያት ሁሉ በተሰበሰቡበት እንጂ። ጥርጣሬው የዐደባባይ እንደነበረ ሁሉ፣ ፈውሱም የአደባባይ መሆን ነበረበት። ጌታችን ሌሎቹ ባሉበት ለቶማስ ብቻ የተናገረው፣ ቶማስ በወንድሞቹ ፊት ክብሩ እንዲመለስ፣ ጥያቄውም በሚታይና በሚዳሰስ መለኮታዊ ምላሽ ተዘግቶ፣ ያ “አላምንም” ያለበት አንደበት በዚያው ጉባኤ መካከል “ጌታዬና አምላኬ” ብሎ እንዲመሰክር ነው።

መላእክት በፊቱ የሚንቀጠቀጡለት፣ ኪሩቤልና ሱራፌል በመፍራት ፊታቸውን የሚሸፍኑለት ክቡር አምላክ፣ አፈርና ትቢያ የሆነው ፍጡር ጣቱን ወደ ጎኑ እንዲያገባ መፍቀዱ እንዴት ያለ ዕፁብ ድንቅ ምሥጢር ነው!

አንድ አፍቃሪ እናት ልጇን ለማሳመን እስከ ልጇ አስተሳሰብ ዝቅ እንደምትለው ሁሉ፤ ጌታም ቶማስ ወደ እምነት እንዲመጣ እስከሚያስፈልገው ጥግ ድረስ ራሱን ዝቅ አደረገ።

ብዙ ጊዜ እኛ ወደ እግዚአብሔር ለመድረስ ረጅም ደረጃዎችን መውጣት ያለብን ይመስለናል፤ ነገር ግን ጌታ ልክ ለቶማስ እንዳደረገው፣ አንተ ባለህበት የድካም፣ የጥርጣሬና የጭንቀት ደረጃ ድረስ ወርዶ ያገኝሃል። አንተ መጸለይ እንኳ በጠፋህ ጊዜ፣ እርሱ በዝምታህ ውስጥ ሆኖ ያናግርሃል፤ ምክንያቱም እርሱ አባት ብቻ ሳይሆን፣ እንደ እናት የሚራራ፣ ድካምህን ተረድቶ ዝቅ የሚል አፍቃሪ ነውና።

ጌታችን ቶማስን ቁስሉን እንዲነካው የጋበዘው ትንሣኤው ምትሐት አለመሆኑን፣ ይልቁንም በመስቀል ላይ የተቸነከረው ያው የተወጋው ሥጋው ከሙታን መነሣቱን በተግባር ለማስረገጥ ነው። የቶማስ እጅ የጌታን ጎን ሲዳስስ፣ የዓለም ሁሉ ጥርጣሬ አብሮ ተዳሰሰ፤ ለትውልድ ሁሉ የሚሆን የማይነቃነቅ የትንሣኤ ማረጋገጫም ሆነ።

“በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን።” (ት.ኢሳ ፶፫፥፭) እንዲል የቶማስ የጥርጣሬው ሕመም ቁስሉን በመዳሰስ ተፈወሰ።

“ጌታዬ አምላኬም ብሎ መለሰለት።” ዮሐንስ ፳፥፳፰

በርግጥም ሌሎች ሰዎች ከሞት ሲነሡ ቶማስ ተመልክቷል። ነገር ግን ቶማስ ጌታችንን ባየ ጊዜ የሰጠው ምስክርነት ከሞት ስለመነሣቱ ብቻ አልነበረም ስለ ተነሣው አካል ምንነት ማለትም ስለ ጌትነቱና የባሕርይ አምላክነቱ መሰከረ እንጂ።

የተመለከተው ቁስል በሕንድ ለሚደርስበት ስቃይ የሚጸናበት፣ እስከሞት ደርሶ ትንሣኤውን የሚመሰክርበት ሆነ።

“ኢየሱስም፦ ስለ አየኸኝ አምነሃል፤ ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው አለው።” ዮሐንስ ፳፥፳፱።

ጌታ ቶማስን “ስለ አየኸኝ አምነሃል” ሲለው፣ እምነቱ በማየትና በመዳሰስ ላይ መወሰኑን መገሠጹ ነው፤ ይህም ተግሣጽ ቶማስን ለማሳፈር ሳይሆን፣ እምነቱ ከሥጋዊ ዓይን እይታ ወጥቶ ወደ መንፈሳዊ ማስተዋል እንዲሸጋገር ለማድረግ ነው።

ምክንያቱም እውነተኛ እምነት “ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፣ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ” (ዕብ. ፲፩፥፩) እንጂ በዓይን እይታ ላይ ብቻ የሚቆም አይደለምና።

ቅዱስ ጴጥሮስ ይህንን ምሥጢር ሲያደንቅ “እርሱንም ሳታዩት ትወዱታላችሁ፤ አሁንም ምንም ባታዩት በእርሱ አምናችሁ፥ በነፍሳችሁ መዳን የማይነገርና ክብር የሞላበት ሐሴት ታደርጋላችሁ” (፩ጴጥ. ፩፥፰) ይላል።

የተወደዳችሁ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሆይ ይህን አስተውሉ። ቶማስ በዓይኔ ካላየሁና በእጄ ካልዳሰስኩ አላምንም ማለቱ የአእምሮው ምርምር በእምነቱ ላይ ገዥ እንዲሆን አድርጎት ነበር። እናንተም በያላችሁበት የትምህርት ዘርፍ የምትቀስሙት ዕውቀት አእምሮአችሁን በትዕቢት አሳብጦ ከፈጣሪያችሁ እንዳያርቃችሁ ተጠንቀቁ።

“እግዚአብሔርን ይህን አሳየኝ ያንን አድርግልኝ፣ ከዛ አምንሀለሁ” ማለት የንግድ ሐሳብ እንጂ እውነተኛ እምነት አይደለም።

ጌታ ቶማስን “ያመንህ እንጂ ያላመንክ አትሁን” (ዮሐ. ፳፥፳፯) ብሎ የገሠጸው፣ እናንተም በአጉል ፍልስፍናና በእግዚአብሔር የለሽ ዕውቀት ታውራችሁ “የማይታየውን መለኮት” እንዳትክዱ ነው።

ቶማስ የጌታን ቁስል እንዲዳስስ የተጋበዘው፣ የእኛ የጥርጣሬና የኃጢአት ቁስል የሚድነው በእርሱ የፍቅር ቁስል ብቻ ስለሆነ ነው። “በእርሱም ቁስል እኛ ተፈወስን” (ት.ኢሳ. ፶፫፥፭) ተብሎ እንደተጻፈ፣ ከዓለም ፍልስፍናና ሳይንስ ይልቅ ከክርስቶስ መስቀል ሥር እውነተኛውን ሰላም ፈልጉ።

እንደ ቶማስ መጠየቅ ቢኖርባችሁ እንኳ፣ ጥያቄያችሁ ወደ “ጌታዬና አምላኬ” ምስክርነት የሚያደርስ እንጂ ወደ ክሕደት የሚያወርድ እንዳይሆን ተጠንቀቁ። ጌታችን ቶማስን በዝምታው ውስጥ እስከ ስምንት ቀን እንደጠበቀው ሁሉ፣ እናንተንም በፈተናችሁ ውስጥ በትዕግሥት ይጠብቃችኋል።

በሕይወት ጉዟችሁ ላይ በርካታ የተዘጉ በሮች ሊገጥሟችሁ ይችላሉ፤ የጭንቀት፣ የጥርጣሬ፣ ወይም የብቸኝነት በሮች። ነገር ግን አስታውሱ፤ ጌታችን በዝግ በር አልፎ ወደ ደቀ መዛሙርቱ እንደገባ ሁሉ፣ ዛሬም ወደ እናንተ ሕይወት ለመግባት በር አይከለክለውም።

​እንደ ቶማስ በሐሳብ ማዕበል ስትናወጡ፣ ዓለም በአጉል ፍልስፍናና በእግዚአብሔር የለሽ ዕውቀት ልባችሁን ስታደነዝዘው፣ ውስጣችሁ በተለያዩ ነገሮች ሲጨናነቅና ሰላምና ተስፋ ስታጡ እርሱ በትዕግሥት ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” ይላችኋል። ቶማስ የጌታን ቁስል ነክቶ የራሱን የጥርጣሬ ቁስል እንደፈወሰ፣ እናንተም በትምህርታችሁም ሆነ በኑሮአችሁ የሚገጥማችሁን ስብራት ይዛችሁ ወደ እርሱ ቅረቡ። የዓለም ዲግሪና ዕውቀት አፈር ሆኖ ሲቀር፣ እናንተ ግን ሳታዩ በማመናችሁ ያገኛችሁት የብፅዕና አክሊል ለዘለዓለም ይኖራል።

የክርስቶስ ሰላም፣ ከምድራዊ ዕውቀት በላይ የሆነው መለኮታዊ ጥበብ፣ በልባችሁና በአእምሮአችሁ ይንገሥ።

ጌታችን በፈተናችሁ መካከል መጽናናትን፣ በጥርጣሬያችሁ መካከል እውነተኛ እምነትን፣ በድካማችሁም ውስጥ የእጆቹን ብርታት ይስጣችሁ።

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ቀዳም_ሥዑር

ከመምህር አዲሱ በዛብህ
የማይሞተው አምላካችን በፈቃዱ ቅድስት ነፍሱን ከሥጋው ከለየ በኋላ ሰማይና ምድር የማይችሉት አምላካችን እኛን ያስነሣ እና ነጻነትን ይሰጠን ዘንድ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ነጻ ሲያወጣ በአካለ ሥጋ ከመለኮቱ ያለመለያየት በመቃብር ሦስት ቀን ሦስት ሌሊት ሙስና መቃብር ሳያገኘው ቆይቷል።
ይህንን ሊቁ ቅዱስ ቄርሎስ ሲያስረዳ እንዲህ ይላል”ነፍሱን በሲኦል አልተወም ሥጋውም ሙስና መቃብርን አላየም መለኮቱ ከሁለቱም አልተለየም ሁለንተናው ከነፍስ ጋር በሲኦል ነበር። በሲኦል ለጻድቃን የምሥራችን አበሠረ፤ ሁለንተናው ከሥጋ ጋር በመቃብር ነበር እንጂ በቦታው ሁሉ ምሉእ ነውና” (ሃይ. አበ ዘቄርሎስ ፸፩፥፲፭-፲፮)
ለሁላችን የማያልፍ ድኅነትን ፣ ሥርየተ ኃጢአትን ፣ ቅድስናን ፣ አሸናፊነትን እና ይቅርታን ይሰጠን ዘንድ ሞታችንን ሞተ፤ የገባልንን ቃል ኪዳን ፈጸመ። “ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደ ነበረ፥ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል።” እንዲል። (ማቴ፲፪፥፵)
ጌታችን ከዐርብ ሠርክ እስከ እሑድ መንፈቀ ሌሊት ድረስ ሦስት ቀን ሦስት ሌሊት በመቃብር ዐርፏል። እነዚህ ቀንና ሌሊት የራሳቸው ትርጉም አላቸው። የነገረ ክርስቶስ መጽሐፍ ጸሐፊ መጋቤ ሐዲስ ክቡር ዶክተር ሮዳስ ታደሰ ስለ ሦስት ምክንያት እንደሆነ ይጠቅሳሉ: –
፩. ለአዳም ፣ ለሔዋን ፣ ለሕፃናቱ ሊክስ
፪. ለሥጋ ፣ ለነፍስ ፣ ለደመ ነፍስ ሊክስ
፫. ሞትን ፣ ፍዳን ፣ ኃጢአትን ሊያጠፋ ጌታችን ሦስት ቀን ሦስት ሌሊት በመቃብር ዐርፏል። (ነገረ ክርስቶስ፡ ገጽ፻፸፰)
ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት
ኢየሱስ ክርስቶስ በከርሠ መቃብር ፫ ቀንና ፫ ሌሊት አደረ፡፡ ይኸውም ነቢዩ ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ እንዳደረው (ት/ዮና ፪÷፩-፪) ራሱም መድኀኔ ዓለም ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በ፫ ኛው ቀን አነሣዋለሁ ብሏል፡፡ (ዮሐ. ፪፥፲-፳፪) የተሰቀለ ዐርብ ፮ ሰዓት፤ ነፍሱን ከሥጋው የለየው ዐርብ ፱ ሰዓት ፤ ወደ መቃብር የወረደው ዐርብ ፲፩ ሰዓት ፤ የተነሣ ቅዳሜ ለእሐድ አጥቢያ ሌሊት ፮ ሰዓት ነው፡፡ ይህ ፫ ቀንና ፫ ሌሊት እንዴት ተባለ? ቢሉ የመጀመሪያው ብርሃኑን “ቀን” ጨለማውን “ሌሊት” በማለት የሚቆጠረው አቆጣጠር ነው፡፡ ይኸውም
ሦስቱ ቀኖች: –
🕕 ዐርብ ከነግህ/ጠዋት እስከ ቀን ፮ ሰዓት ብርሃን ነበር
🕘 ከ፱ ሰዓት እስከ ሰርክ ብርሃን ነበር
🕛 ቅዳሜ መዐልት/ቀን

  ሦስቱ ሌሊቶች: -

🕕 ዐርብ ከቀን ፮ ሰዓት እስከ ቀን ፱ ሰዓት አምላክ በመስቀል ላይ ሳለ ጨለማ ሆነ
🕛 ዐርብ ለቅዳሜ ሌሊት
🕛 ቅዳሜ ለእሁድ ሌሊት
ሌላው በዕብራውያን የቀን አቆጣጠር መሠረት ዓርብ ሌሊቱን እሑድ ቀኑን ይስቡና ይቆጠራል፡፡ 
ይኸውም: – ሌሊቶቹ
ሐሙስ ለዐርብ 
  ዐርብ ለቅዳሜ
  ቅዳሜ ለእሑድ
ቀኖቹ ደግሞ 
  ዐርብ ቀኑን
 ቅዳሜ ቀኑን
እሁድ ቀኑን ቆጥሮ ነው፡፡
ጌታችን ቀድሞ አዳምን፤ ሔዋንን ዐርብ ፈጥሮ ቅዳሜ እንዳረፈ ሁሉ አሁንም ያጡትን ገነትን ባጡበት ዐርብ ዕለት ሰጥቶ ቅዳሜ በመቃብር አርፎባታል ስለዚህም የተለየችቅዳሜናት።
➢ አራቱ ስያሜዎች፦
፩. ቀዳም ሥዑር
ሥዑር ማለት የግእዝ ግስ ሆኖ በአማርኛ የተሻረ ማለት ሲሆን በአንድ ላይ ሲነበብ የተሻረ_ቅዳሜ የሚል ትርጓሜ እናገኛለን። ምክንያቱ እንደ ቀደመቺቱ ሰንበት የማናርፍባት ይልቁንም ደቀመዛሙርቱን አብነት አድርገን በጾም በኀዘን ሕማሙን እያሰብንባት የምናሳልፋት ቀን በመሆኗ ቀዳም ሥዑር ተብላለች።
፪. ዐባይ ሰንበት
አምላካችን ሃያ ሁለቱን ሥነ ፍጥረት ፈጥሮ እንዳረፈባት የማዳኑንም ሥራ በመስቀል ላይ ፈጽሞ በአዲስ መቃብር ዐርፎ ውሎባታልና ዐባይ ሰንበት ተብላለች።
፫. ቅዱስ ቅዳሜ
በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን አድኖባታል ፣ ሲኦልን በዝብዟል ፣ ምርኮን ለራሱ ጨምሯል ፣ ዲያብሎስን አሳፍሯል ፣ የዕዳ ደብዳቤያችንን ደምስሷል ከሌሎች ቀናት ሁሉ የተለየች በመሆኗ ቅዱስ ቅዳሜ ተብላለች።
፬. ለምለም ቅዳሜ
በዚህ ዕለት በኖኅ ዘመን የጥፋቱ ውኃ ማለቁን የሰላም አብሣሪ ርግብ ለኖኅ ቄጤማ እንዳመጣችለት አሁንም የጥፋቱ ሞት ራቀልን ፣ ከሞት ወደ ሕይወት ተሸጋገርን ፣ አንቀጸ ገነት ተከፈተልን ሲሉ ካህናት አባቶቻችን የቅዳሜው የነግህ ጸሎት ከተጠናቀቀ በኋላ ለምእመኑ ለምለም ቄጤማ ስለሚሰጡ እኛ ምእመናንም በግንባራችን ላይ አድርገን ትንሣኤውን ስለምናከብር ለምለም ቅዳሜ ተብላለች።

ዐርብ ዕለተ ስቅለት

ከመምህር አዲሱ በዛብህ

ዕለተ ዓርብ በቤተክርስቲያን ልዩ ቀን ነው፡፡ የማይታመመው ታሞ የዋለበት፣ የወደቁ ከተረሱበት ከትቢያ የሚያነሳ እሱ ሲወድቅ ሲነሳ የዋለበት፣ ሕመምተኞችን የሚፈውስ እሱ ሲያቃስት የዋለበት፣ ከሲኦል የዲያብሎስ ግብር ነፃ የሚያወጣ ሲገረፍ የዋለበት፣ ወልደ እግዚአብሔር ለወዳጆቹ ድኅነት በመሥዋዕትነት ሙሽራ የሆነበት የደስታ ቀን፤ አሳዳጅ አሳሪያችን ዲያብሎስ ከነወጥመዱ ድል የተነሳበት ቀን ነው። ከዚህም የተነሳ በቤተክርስቲያን የተለያየ ምሥጢራዊ ስያሜዎች ተሰጥቶታል፡፡
የስቅለት ዓርብ ይባላል።
የዓለም ሁሉ መድኃኒት የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ ለዓለም ድኅነት መሥዋዕት ሆኖ የዋለበት ዕለት በመሆኑ የስቅለት ዓርብ ተብሏል። (ማቴ ፳፯፥፴፭)
መልካሙ ዓርብ ይባላል።
ይህም የሚያስገነዝበን ከስቅለተ ክርስቶስ በፊት ማንም ሰው ሲያጠፋ በመስቀል ተሰቅሎ እንዲሞት ይደረግ ነበር፤ በተለይ በሮማውያንና በፈሪሳውያን ሕግ መስቀል የወንጀለኞች መቅጫ ነበረ። በዚህ ዕለት ግን ታሪክን የሚቀይር ነገርን የሚገለብጠው አምላክ የወንጀለኞች መቅጫ ምልክት የነበረውን መስቀል በደሙ ቀድሶ የምሕረት ምልክት፣ የሕይወት አርአያ፣ የዲያብሎስ ድል መንሻ ፣ የቤተክርስቲያን ጌጥ የገዳማት ዘውድ ስላደረገው እንዲሁም በዕለተ ዓርብ በሞቱ ሕይወትን ስላገኘን መልካሙ ዓርብ ተብሏል፡፡
➣ ጌታችን ከ፮-፱ ሰዓት በመስቀል ላይ ሳለ የተናገራቸው ፯ቱ ቃላት
፩ኛ. ኤሎሄ ኤሎሄ ኤልማስ ላማ ሰበቅታኒ፤ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ። (ማቴ. ፳፯፥፵፮)
፪ኛ. እውነት እውነት እልሃለሁ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትኖራለህ፡፡ (ሉቃ. ፳፫፥፵፫)
፫ኛ. አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ፡፡ (ሉቃ. ፳፫፥፵፮)
፬ኛ. አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው። (ሉቃ. ፳፫፥፴፬)
፭ኛ. እናትህ እነኋት፤ እነሆ ልጅሽ፤ (ዮሐ. ፲፱፥፳፮-፳፯)
፮ኛ. ተጠማሁ። (ዮሐ. ፲፱፥፴)
፯ኛ. ተፈጸመ ። (ዮሐ. ፲፱፥፴)
➣ ጌታችን ከ ፮-፱ ሰዓት በመስቀል ላይ ሳለ የተፈጸሙ ፯ቱ ተአምራት፤
፩ኛ. ፀሐይ ጨለመች።
፪ኛ. ጨረቃ ደም ሆነች።
፫ኛ. ከዋክብት ረገፉ።
፬ኛ. የቤተመቅደስ መጋረጃ ለሁለት ተከፈለ።
፭ኛ. ዐለቶች ተሰነጣጠቁ።
፮ኛ. መቃብራት ተከፈቱ።
፯ኛ. የሞቱት ተነሡ። (ማቴ. ፳፯፥፵፭-፵፮)
፭ቱ ቅንዋተ መስቀል ችንክሮች ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ እና ሮዳስ ይባላሉ።
➣ ሞትን ይሽረው ዘንድ የማይሞተው ሞተ፤ መከራንም ታገሰ።
➣ ሁሉን የያዘውን እርሱን ያዙት።
➣ ሁሉን የሚገዛውን እርሱን አምላካችንን እጅ አሰሩት።
➣ ሐጢአትን ይቅር የሚል እርሱን ሐጢአተኛ አሉት።
➣ የማይገረፍ አምላክ እርሱን የሰውን ሥጋ በመዋሐዱ ገረፉት።
➣ እንደ መብረቅ የሚያንፀባርቀውን ነጭ ልብስ የሚያለብስ አምላክ እርሱን ቀይ ግምጃ አለበሱት።
➣በእሳት በተጋረዱ ዙፋን ላይ የሚቀመጥ እርሱን በመዘባበቻ ወንበር ላይ አስቀመጡት።
➣እንደ ድንኳን ሰማይን የዘረጋ እርሱን በመስቀል ላይ ሰቀሉት።
➣የመላእክትን አለቆች በፊቱ በመፍራት የሚቆሙለት እርሱን በጲላጦስ ፊት አቆሙት።
➣በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈርድ እርሱን እንደበደለኛ ተፈረደበት።
➣አለምን ሁሉ በቅፅበት የፈጠረ እርሱ በመለኮቱ ሕያው ሆኖ በሥጋው ሞተ።
ጌታችን፣ መድኃኒታችን፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶ በሦስተኛው ቀን ሞትን ድል አድርጎ ተነስቶ ከኃጢአት ቁራኝነት፣ ከዲያብሎስ ባርነት ነፃ አውጥቶናል። እኛስ በሞቱ የዳንን ልጆቹ መንግሥቱን ለመውረስ ምን ልናደርግ ይገባናል?
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለእኛ መሞቱና መነሳቱ የመዳን መንገድን ከፍቶልናል፤ ነገር ግን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እኛም እርሱን አብነት ድርገን ያዘዘንን ሁሉ መፈጸም ይገባናል።
➣ ልናደርጋቸው የሚያስፈልጉን ነገሮች ፦
1.እምነት እና ንስሐ
በእግዚአብሔር በሙሉ ልብ ታምነን ከኃጢአታችን ልንጸጸትና ልንመለስ ይገባል። መጽሐፍ እንዲህ ይላልና፤ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ”። (ማቴ. ፫፥፩)
2. ቅዱስ ሥጋውን ክቢር ደሙን መቀበል
በጥምቀት (ከውኃና ከመንፈስ/ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና ከማኅጸነ ዮርዳኖስ) መወለድ “ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔርን መንግሥት ማየት አይችለም” (ዮሐ. ፫፥፫) እንዲል።
ቅዱስ ቁርባንን (ቅዱስ ሥጋናውን፣ ክቡር ደሙን) መቀበል ያስፈልጋል። “ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው” (ዮሐ. ፮፥፶፬) እንዲል።
3. ትእዛዛትን መጠበቅ
➣ እግዚአብሔርን በሙሉ ልብ መውደድ፤ “እግዚአብሔር አምላክህን በፍጹም ልብህ፥ በፍጹም ሰውነትህ፥ በፍጹም ኀይልህ፥ በፍጹም ዐሳብህ ውደደው፤” ። (ሉቃ. ፲፥፳፯ ፣ ዘሌዋ. ፲፱፥፲፰)
➣ ሰውን እንደ ራስ መውደድ፤ “ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ፤” (ዘሌዋ. ፲፱፥፲፰)
➣ ዐሥርቱ ትእዛዛትን መጠበቅ፤ “ብትወዱኝ ትእዛዛቴን ጠብቁ፤” (ዮሐ. ፲፭፥፲፬)
4. መጾምና መጸለይ
” ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ፤ መንፈስ ይሻልና፤ ሥጋ ግን ደካማ ነው” (ማቴ. ፳፮፥፵፩)
ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን ያስተማረን፣ አብነት የሆነን አምላክ ነውና በሁሉ ነገር እርሱን ልንመስለው ይገባናል። ̏ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና˝ (ዮሐ. ፲፫፥፲፭)
5. መልካም ሥራ መሥራት
በቅዱስ ወንጌል የተጻፈልንን በሕይወት መኖር አለብን።
ድሆችን መርዳት፣ የተራቡትን ማብላት፣ የተጠሙትን ማጠጣት ፣ የታረዙትን ማልበስ፣ … እነዚህንና የመሳሰሉትን የትሩፋት ሥራዎችን ልንተገብራቸው ያስፈልጋል። (ማቴ. ፳፭፥፥፴፩-፵፮)
➣ ምሕረትና ትሕትና መልበስ
ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ የእጆቹ ፍጥረቶች አይሁድ ያን ሁሉ መከራ ሲያደርሱበት ጊዜ እፍ ብሎ ማጥፋት እየቻለ በዝምታ መከራውን ተቀብሏል፤ እንዲሁም በግፍ ለሰቀሉት አባት ሆይ የሚያደርጉትን ያውቁምና ይቅር በላቸው። (ዮሐ. ፲፱፥፩-፳፪) ፣ (ሉቃ. ፳፫፥፴፬)
6. ትዕግሥት እና ቅድስና
ፈተናን በእምነት መቋቋምና ራስን ከኃጢአት ማራቅ ያስፈልጋል።
“እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተ ቅዱሳን ሁኑ” (ዘሌዋ. ፲፱፥፪፣ ፩ኛ ጴጥ. ፩፥፲፭) እንዲል በቅድስና መንገድ ልንመላለስ ያስፈልጋል።
➣ በአጭሩ መንግሥተ ሰማያት በእምነት ብቻ ሳይሆን እምነት + ሥራ + ጸጋ የሚወረስ ነውና እምነትን ከምግባር ጋር አስተባብረን ልንይዘው ያስፈልጋል።
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር

ጸሎተ ኀሙስ

ከመምህር አዲሱ በዛብህ
ከስቅለትና ከትንሣኤ በፊት በሕማማት ሳምንት ያለው ሐሙስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ልዩ ልዩ ስያሜዎች አሉት፡፡ እነዚህንም ስያሜያት እንደሚከተለው እንመለከታለን።
ሀ. ጸሎተ ሐሙስ ይባላል።
የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ይለምን ይማልድ የነበረን ሥጋ የተዋሐደ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው መሆኑን ለማጠየቅ እንዲሁም ለአርአያነት ጠላቶቹ መጥተው እስኪዙት ድረስ ሲጸልይ በማደሩ ምክንያት ይህንን ስያሜ አገኘ። (ማቴ ፳፮፥፴፮-፵፮፣ ፲፯፥፩)
ለ. ሕጽበተ እግር ሐሙስ ይባላል።
ሕጽበተ እግር፦ ይህ ስያሜ የተሰጠው ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀመዛሙርቱን እግር በማጠቡ ምክንያት ነው፤ ይህም የሚያሳየው የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ መሆኑን ነው፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ካህናት በተለይም ሊቃነ ጳጳሳትና የደብር አስተዳዳሪዎች በመካከላችን ተገኝተህ የእኛንና የሕዝብህን ኃጢአት እጠብ ሲሉ ከአገልጋዮቹ ጀምረው በቤተክርስቲያን የተገኙትን ምእመናን እግር በወይንና በወይራ ቅጠል ሲያጥቡ ያረፍዳሉ፡፡
ሐ. የምሥጢር ቀን ይባላል።
ከሰባቱ ምሥጢራት አንዱ በዚህ ዕለት ተመሥርቷልና፤ ይኸውም ‹‹ይህ ስለእናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው፡፡ እንካችሁ ብሉ›› ጽዋውንም አንሥቶ አመሰገነ፤ ‹‹ይህ ስለእናንተ ነገ በመስቀል የሚፈስ ደሜ ነው ከእርሱ ጠጡ›› በማለት እኛ ከእርሱ ጋር፣ እርሱ ከእኛ ጋር አንድ የምንሆንበትን መንገድ ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ስያሜ ነው፡፡
በዚህ ዕለት ቅዳሴ ይቀደሳል፤ የሚቀደሰውም በለሆሳስ ሲሆን እንደ ቃጭል ሆኖ የሚያገለግለውም ጸናጽል ነው፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን ለመያዝ ሲመጡ ድምጻቸውን ዝቅ አድርገው፣ በለሆሳስ እየተነጋገሩ መምጣታቸውን ለማሰብ ነው፤ በቅዳሴውም ጸሎተ ተአምኖ፣ ኑዛዜ አይደረግም፤ ሥርዓተ ቁርባን ግን ይፈጸምበታል፤ ይህም ጌታችን የሰጠውን ዘለዓለማዊ ቃል-ኪዳን ለማሰብ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሓ ታጥቦ ተዘጋጅቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል ይኖርበታል፡፡
መ. የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል።
ጸሎተ ሐሙስ (የፋሲካ እራት) ፦ ምክንያቱም መሥዋዕተ ኦሪት ማለትም በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጐ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ነው፡፡ ‹‹ይህ ጽዋዕ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን ሐዲስ ኪዳን ነው፡፡ ከእርሱም ጠጡ›› በማለቱ ይታወቃል፡፡ (ሉቃ.22፥20) ኪዳን ማለት በሁለት ወገን መካከል የሚደረግ ውል፣ ስምምነት፣ መሐላ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ጌታችን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ዘለዓለማዊ ቃል-ኪዳን በራሱ ደም የፈጸመበት ዕለት መሆኑን በማሰብ የቃል-ኪዳኑ ፍጻሜዎች፣ ጠባቂዎች መሆን እንደሚገባን እንማራለን፡፡
ሠ. አረንጓዴ ሐሙስ ይባላል።
አምላካችን የጸለየበትን የአትክልት ቦታ ወይም ጌቴሴማኒ ለማሰብ ይህ ስያሜ ተሰጥቶታል።
ጌታ እንዴት፣ ምን እና ለምን ጸለየ?
እንዴት ጸለየ?
አምላካችን የምሥጢር ሐዋርያቱን (ዮሐንስ ፣ ያዕቆብ እና ጴጥሮስ) አምስት ትእዛዛትን (ተቀመጡ ፣ ትጉ ፣ ጸልዩ ፣ ተኙ ፣ ዕረፉ) በማዘዝ ግንባሩን ምድር አስነክቶ ሰግዶ ጸለየ።(ማቴ፳፮፥፴፮-፵፭)
ምን ጸለየ?
ሦስት ጊዜ ደጋግሞ የጸለየው ጸሎት አንድ ዓይነት ነው ይኸውም: – “አባቴ ቢቻልስ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፤ ነገር ግን አንተ እንደምትወድ ይሁን እንጂ እኔ እንደምወድ አይሁን አለ።” (ማቴ፳፮፥፴፮-፵፭)
ለምን ጸለየ?
፩. ምሣሌ ይሆነን ዘንድ ነው።
፪. ፈቃዱን ማስቀደም እንዳለብን እናውቅ ዘንድ ነው።
፫. ወደፈተና እንዳንገባ መጸለይ እንደሚገባ እናውቅ ዘንድ ሊያስተምረን ነው።
➣ የጸሎቱ ትርጓሜ ምንድ ነው?
፩. ዓለም እንድትድን እና ክብርን እንድታገኝ ለሞት ተላልፎ እንደሚሰጥ ገልጿል።
“ያለ እኔ ሞት የዓለሙ ድኅነት ያለ እኔ ሐሳር የዓለሙ ክብር አይቻልም እንጂ የሚቻልስ ከሆነ ይህ ጽዋዕ ሞት ይለፍልኝ። ነገር ግን ያንተ ፈቃድ ይደረግ እላለሁ እንጂ የእኔ ፈቃድ ይደረግ አልልም።” (ወንጌል አንድምታ ገጽ ፪፻፸፱)
፪. ሞት እንዲቀርልን እንደ ሞተ ገልጿል። “በእኔ ሞት የዓለም ድኅነት በእኔ ኃሣር የዓለም ክብር የሚቻልስ ከሆነ እኔ ከሞትሁላቸው ከእኔ ሞት የተነሳሣ ይህ ጽዋዕ ሞት ይቅርላቸው። (ወንጌል አንድምታ ገጽ፪፻፸፱)
፫. አብነት ይሆነን ዘንድ ሞትን እንደሚቀምስ ገልጿል። ” ከእኔ ለምዕመናን ይለፍላቸው ። እኔን አብነት አድርገው ይሙቱ ። ነገር ግን የእኔ ፈቃድ ካንተ ፈቃድ ልዩ ሁኖ የእኔ ፈቃድ ይሁን አልልም። የእኔ ፈቃድ ካንተ ፈቃድ ጋራ አንድ ነውና ያንተ ፈቃድ ይሁን እላለሁ እንጂ። ” (ወንጌል አንድምታ ገጽ፪፻፸፱)
➣ በዚህ ዕለት በወንጌላት የተመዘገቡ ድርጊቶችን ቀጥለን እንመልከት፦
ሀ. የፋሲካ ዝግጅት የተደረገበት ዕለት ነው።
ዝግጅቱ በሦስቱ ወንጌላት ላይ ተመዝግቧል፡፡ ማቴ. ፳፮፥፲፯-፲፱ ማር. ፲፬፥፩-፲፮፣ ሉቃ. ፳፪፥ ፮-፲፫)
ፋሲካ ማለት ማዕዶት ፣ መሻገር ፣ ማለፍ ማለት ነው፤ ይኸውም እሥራኤላውያን በግብጽ ምድር ሳሉ መልአኩን ልኮ እያንዳንዱ እሥራኤላዊ የበግ ጠቦት እንዲያርድና ደሙን በበሩ ወይንም በመቃኑ እንዲቀባ ለሙሴ ነገረው፤ ሙሴም ለሕዝቡ ነገረ፤ ሁሉም እንደታዘዙት ፈጸሙ፤ መቅሠፍት ከእግዚአብሔር ታዞ መልአኩ የደም ምልክት የሌለበትን የግብጻውያን ቤት በሞተ በኵር ሲመታ፤ የበጉ ደም የተቀባውን የእሥራኤላውያንን ቤት ምልክቱን እያየ ማለፉን ለማመልከት ነው፡፡ (ዘዳ.12፤1-13) በዚህ መነሻነት በየዓመቱ እሥራኤላውያን በመጀመሪያ ወራቸው በዐሥራ ዐራተኛው ቀን በግ እያረዱ የፋሲካን በዓል ያከብራሉ፡፡ ሀገራችንም አስቀድማ ብሉይ ኪዳንን የተቀበለች ሀገር እንደመሆኗ ይህ ድርጊት ይፈጸምባት ነበር፡፡ በአንጻሩም ዛሬ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ፋሲካ ተብሎ የተጠራበት ምክንያት በዚህ በፋሲካ በዓል ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ደሙን ስላፈሰሰልን ነው፡፡ በደሙ መፍሰስ ሞተ በኵር የተባለ ሞተ ነፍስ ቀርቶልናልና፤ ‹‹ፋሲካችንም ክርስቶስ ነው፡፡›› (1ኛቆሮ. ፭፥፮፣ 1ኛ ጴጥ. ፩፥፲)
ለ. በዚህ ዕለት እንደ ማክሰኞ ለደቀመዛሙርቱ ረጅም ትምህርት አስተምሯል።
ምሥጢረ ሥላሴ (የሦስትነት ትምህርት) ፤ ምሥጢረ ሥጋዌ (የአምላክ ሰው መሆን) ፤ (ዮሐ. ፲፬፥፲፮) የሚገኘው በጠቅላላ የዚህ ዕለት ትምህርት ነው፡፡ የትምህርቱም ዋና ዋና ክፍሎች ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንና የዳግም ምጽአቱ ነገር ነው፡፡ እነዚህም በስፋትና በጥልቀት መማር እንደሚገባ ሲያስረዳን በተአምራት ሊገልጥላቸው ሲችል በረጅም ትምህርት እንዲረዱት አድርጓል፡፡ ተማሪዎቹን እሱ እያስተማራቸው ሳለ ያልገባቸውን እየጠየቁ ተረድተዋል፡፡ ከዚህም እያንዳንዳችን በቤተክርስቲያን ተገኝተን መማርና ያልገባንን ጠይቆ መረዳት እንደሚገባን እንማራለን፡፡
ሐ. ይህ ዕለት ከደቀመዛሙርቱ አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታ ሆይ፣ መምህር ሆይ ብሎ በመሳም አሳልፎ የሰጠበት ዕለት ነዉ።
ጭፍሮቹም በዚሁ ዕለት ሌሊት የክብር ባለቤት የሆነውን ጌታችንን ይዘው ወደፊት፣ ወደኋላ እየጐተቱ፣ እያዳፉ ወደ ሊቀ ካህናቱ ወደ ቀያፋ ወስደውታል።
የመዝሙረ ዳዊት ምንባባት
በአንድ ሰዓት፡- “አፉ ከቅቤ ይልቅ ለዘበ፤ በልቡ ግን ሰልፍ ነበረ፤ ቃሎቹም ከዘይት ይልቅ ለሰለሱ፤ እነርሱ ግን እንደ ተመዘዘ ሰይፍ ናቸው” (መዝ፶፬፥፳፩)
በሦስት ሰዓት፡- “የጻድቅን ነፍስ ያደቡባታል፤ በንጹህ ደምም ይፈርዳሉ፡፡” (መዝ፺፫፥፳፩)
በስድስት ሠዓት፡- “የብዙ ሰዎችን ስድብ ሰምቻለሁና በዙሪያው ፍርሃት ነበረ በላዬ በአንድነት በተሰባሰቡ ጊዜ፤ ነፍሴን ለመንጠቅ ተሰባሰቡ፡፡” (መዝ ፴፥፲፫)
በዘጠኝ ሰዓት፡- “እግዚአብሔር እረኛዬ ነው፤ የሚያሳጣኝም የለም፤ በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፡፡” (መዝ. ፳፪፥ ፩-፪)
ኅጽበተ እግር፣ ሲጀመር ደግሞ “በሂሶጵ እርጨኝ እነጻማለው እጠበኝ ከበረዶም ይልቅ ነጭ እሆናለው፡፡” (መዝ ፶፥፯)
በመጽሐፈ ግብረ ሕማማት፡- “ከዚህ በኋላ የእግር እጥበት ሥርዓት ነው፤
ዲያቆን ሁለት ኲስኲስቶች ያቅርብ በውስጣቸውም ውኃ ይምላባቸው አንዱ ለእጅ መታጠቢያ እንዲሆን ካህኑም እስከ መጨረሻው ጸሎተ አኮቴት ይበል።
ጸሎተ ዕጣኑንም ደግሞ ዕጣንን ያሳርግ፤ ስለ ሰላም ስለ ሊቀ ጳጳሳት ስለ ማኅበር ይጸልይ፡፡ ሕዝቡም ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን ይበሉ፡፡ አቡነ ዘበሰማያትም ይበሉ ፤ ኀምሳኛውንም የዳዊትን መዝሙር ይበሉ፡፡” (ግብረ ሕማማት ገጽ ፭፻፵፪)
“ከዚህ በኋላ ሕዝቡ ይነሱ አርባ አንድ ጊዜ ኪራላይሶን ይበሉ፤ ካህኑም መስቀል ይዞ ውኃውን ሦስት ጊዜ አሐዱ አብ ቅዱስ (ልዩ ክቡር ንጹሕ ጽኑዕ ነው) ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ (ልዩ ክቡር ንጹሕ ጽኑዕ ነው) ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ (ልዩ ክቡር ንጹሕ ጽኑዕ ነው) እያለ ሦስት ጊዜ ውኃውን ይባርክ፡፡” (ግብረ ሕማማት ገጽ ፭፻፶፱)
“ከዚህ በኋላ ካህኑ እንደ ሥርዓቱ ኅጽበተ እግርን ያድርግ (ይፈጽም) ከዚህ በኋላም ጥቁር ልብስ ለብሰው ሥርዐተ ቅዳሴውን ይጀምሩ የቃጭል ድምጽንም አያሰሙ፡፡” (ግብረ ሕማማት ገጽ ፭፻፷፩)
በአሥራ አንድ ሰዓት፡- “በፊቴ ገበታን አዘጋጀህልኝ በጠላቶቼ ፊት ለፊት ራሴን በዘይት ቀባህ ጽዋዬም የተረፈ ነው” (መዝ. ፳፪፥ ፭-፮)
የአይሁድ ካህናት ያለበደል እና ያለጥፋት ንጹውን ክርስቶስን ለመስቀል ሞት እንዲደርስ በጭካኔ በዕለተ ሐሙስ ከሌሊቱ 3፡00 ጀምሮ ብዙ መከራ አደረሱበት እጅጉን ተሠቃየ፤ እያዳፉ አንዳች ሳይናገር አሠቃዩት ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ በትንቢት መነጽር የተመለከተውን የጌታችንን ሥቃይ እንዲህ ሲል ያመጣዋል፤
“ተጨነቀ፣ ተሠቃየም አፉንም አልከፈተም ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት በሸላቾቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ በማስጨነቅና በፍርድ ተወሰደ ስለ ሕዝቤ ኃጢአት ተመቶ ከሕያዋን ምድር እንደተወገደ ከትውልዱ ማን አስተዋለ? ከክፉዎቹም ጋር መቃብሩን አደረጉ…” እንዲል (ኢሳ፶፫፥፩-፰)
እንበለ ደዌ ወሕማም እንበለ ፃማ ወድካም አመ ከመ ዮም ያብጽሐነ ያብጽሕክሙ ለብርሃነ ትንሣኤሁ እግዚአብሔር በፍስሓ ወበሰላም አሜን! ፤ ያለ ደዌና ያለ ሕማም ያለ ፃማና ያለ ድካም እግዚአብሔር ለትንሣኤው ብርሃን እንደ ዛሬ ቀን በደስታና በፍቅር በአንድነት ያድርሰን ያድርሳችሁ አሜን!

ረቡዕ

ከመምህር ተሾመ ግዛው

እያንዳንዱ የሰሙነ ሕማማት ዕለታት ስያሜ እንዳላቸው ዕለተ ረቡዕም ራሱን የቸለ ምሥጢራዊና ታሪካዊ ትርጒም አለው፡፡ ይህም እንደሚከተለው በዝርዝርእንመለከታለን።
የምክር ቀን (ምክረ አይሁድ)
አይሁድ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስሰ ክርስቶስን የሚይዙበትን መንገድ ይፈልጉ ነበር፤ በመካከላቸው ምንም ዓይነት ልዩነት እንኳን ቢኖር ለኃጢአት ሥራ ግን ተባበሩ፡፡ ፰ት ለተለያየ አላማ የተቋቋመ ማኅበር (ስምንቱ ቤተ አይሁድ) ፦ ሊቃነ ካህናት፣ መገብተ ምኲራብ፣ ኃጥኣን መጸብሓን፣ ጸሓፍት ፈሪሳውያን፣ ሰዱቃውያን፣ ረበናት (መጽሓፈ ሰዓታት ንባቡና ትርጓሜው ሮዳስ ታደሰ ገጽ ፬፻፸፭)
ረበናት የሕዝቡን ሃይማኖታዊና ባሕላዊ ዕሤት ይጠብቃሉ ተብለው የተሾሙ ነበሩ፤ ነገር ግን ሕዝቡን ከመጥቀም ይልቅ የሚጎዳ ተግባር ላይ ተጠመዱ፤ ንጉስ ክርሰቶስን ለመስቀል በእለተ ረቡዕ ተማከሩ፤ ደሙም በላያቸው ላይ እንዲሆን በራሳቸው ላይ የሞት ፍርድን ፈረዱ። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እንደ ገለጸው ‹‹ማኀበራነ አይሁድ ተመድበሉ ለሰቂለ አምላክ ተማሐሉ፣ የአይሁድ ማኅበራት ተሰባሰቡ አምላክን ለመስቀል ተማማሉ›› ይች ዕለት የአዳም የመዳን ተስፋ፣ የነቢያት ትንቢታቸው ፍጻሜ እንዲያገኝ በቤተ አይሁድ ምክር የጸናበት እንዲሁም ለጨለማ አበጋዞች የኀዘን ዳራ የሰፋበት ነው፡፡
በዚህ ዕለት ጌታ ለሞት ተላልፎ እንዲሰጥ አይሁድ መክረው የተነሱበት አንዲሁም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእጃቸው የሚወድቅበት መንገድ ከይሁዳ ጋር ዘዴ የዘየዱበት ዕለት በመሆኑ የቤተ ክርስቲያነችን ሊቃውንት ዕለቱ ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዐመቱን ሙሉ በጾም እንዲታሰብ ሠርዓት ሠርተዋል።
የንስሓ ዕለት
ንስሓ ለሰው ልጅ ከበድል የሚነጻበት የነፍስ ሳሙና ነው፡፡ ቅዱሰ ኤፍሬም ሰለንስሓ እንዲህ ይለናል ‹‹ጌታ ሆይ ወርቅ ትሰጠኝ ዘንድ አለምንህም ወርቅ ክፉዎች የሚፈልጉት ንዋይ ነውና፡፡ ሀብትና ንብረትም አልለምንህም፤ እነርሱም ድኅነትን የሚያስገኙ አይደሉም፡፡ ይቅርታን ማግኘት ከወርቅ ይልቃል፡፡››
ጌታቾን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሠራቸው ድንቅ ሥራዎች ቅዱስ መጽሐፍ ማርያም ባለ ሽቶዋ በሚንቋትና ኃጢአተኛነቷን በየሄዱበት በሚመሰክሩባት ሴት ይቅርታን ያደረገበት ቀን ነው፡፡
ከቀናት ሁሉ ቅዱስ ተብለው የሚጠሩ ዕለታት ነፍስና ሥጋን የሚያነጹ ልዩ ዕለታቶች አሉ፡፡ ማርያም ለንስሓ የተነሳችበት ዕለት ከሌላው ጊዜ በተለየ ሁኔታ በኀዘንና በትካዜ የውስጧን ማንነት የሚያሳያትን በዓይነ ኅሊና ፊት እንጅ ለኃጢአትና ለበደል በሚያቆማት መስታወት ፊት ብቻ አልነበርም፡፡
ከዓይነ ሥጋ ዕይታ በመውጣት በዓይነ ኅሊና የታያት የክብር ዙፋን በመናፈቅ ውድና ክቡር የሆነ ሽቱ ፍለጋ ነበር የወጣችው፤ በወጣችበት ጊዜም ቀላል የማይባል ፈተና ገጥሟት ነበር፡፡ እርሱን ተቋቍማ ነገሥታት ይቀቡት የነበረውን እጅግ የከበረ ልዩ ሽቱ ፍለጋ ተንከራተተች፤ ፈልጋም ባገኘች ጊዜ በውድ ገንዘብ ገዛችው፡፡
የሽቱ ታሪክ በቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ይተረካል፡-
ሰባ ሰገል ለሕጻኑ የገበሩት ከጥንት አባቶቻቸው የመጣ ታሪክ እንዳለው ሁሉ ሽቱውም ልዩ ታሪክ አለው፡፡ ዳዊትና ሰሎሞን ይቀቡት የነበረዉ ውድ ሽቱ ሳይሆን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በወርኀ ስደቷ ጥጦስና ዳክርስ የተባሉ ሽፍቶች ነበሩ፤ እነዚህ ሽፍቶች የሕጻኑን ልብስና ጨማ ከዘረፉ በኋላ ፈያታዊ ዘየማን ሕጻኑን በመታቀፍ ሸኝቶት ነበር፤ የሕጻኑ ወዝም በሽፍታው ልብስ ይቀራል፤ ልዩ ጠረንም ነበረው፤ እንድታጥብለትም ለእናቱ ሲሰጣት ሽታው እስካሁን ከምታውቀው ሽቱ ሁሉ የተለየና በአንድ ተራ ሰው ቤት ሊገኝ የማገባው መሆኑን አውቃ ለነጋዴ ሸጠችው፤ ያ ነጋዴም የሚገዛው ሰው እስኪያገኝ ድረስ በልዩ ቦታ አስቀምጦት ነበር፤ ማርያም እንተ ዕፍረት በመጣች ጊዜ በውድ ዋጋ ሸጠላት፡፡
ማርያም እንተ ዕፍረት ይህንን የገዛችው ሽቱ ለክርሰቶስ እንዲገባ ዐውቃ የስምዖንን ዛቻና ግፊት ሳይበግራት በጽናት ተቋቍማ ወደ ክርስቶስ ቀርባ በፊቱ አቀረበችለት፡፡ በዐይኖቿም ዕንባ አፍሳ እግሮቹን አጠበችው፤ በዕንባዋ ያጠበችው እግሮቹም በጨርቅ ሳይሆን በውብ ፀጉሮቿ ነው እግሮቹን ያበሰችው፡፡
ያን ጊዜ ማርያም እንተ ዕፍረት በጌታ ዘንድ ከእንባዋ የተነሳ ይቅርታን አገኘች፤ ከበደል እስራትም ተፈታች፤ ከ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስትም ተቆጠረች፤ በቅዱሱ ዕለትም ቅድስናን ተቀበለች፡፡ (ሉቃ. ፯፥፴፯-፶)
ማርያም እንተ ዕፍረት እግዚብሔር የሰጣትን ውበትና መልክ ለቅድስና ሳይሆን ለኃጢአት አውላው ነበርና፤ ብዙዎቹ በእርሷ ውበት ተማርከው ገንዘባቸውን ጨረሱ፤ ትዳራቸውን አፈረሱ፤ ክቡር የሆነውንም የክርስቶስ ቤተ መቅደስ አረከሱ፤ በኃጢአት ዓለም እራሳቸውን አዋረዱ፤ ማርያም ግን ከዚህ ሁሉ ጥፋትና በደል በኋላ ወደ ቀልቧ ተመለሰች፤ ሁሉም ከንቱ መሆኑና በሚያልፈው ዓለም የማያልፈውን ክብር መግዛት ፈለገች፡፡
በማርያም እንተ ዕፍረት የሚከተሉትን የሕይወት ለውጥ እንመለከታለን፡-
ለኃጢአት ትጠቀመው የነበረውን መስታወት ለጽድቅ ማያ አደረገቸው፤
ለዝሙት ይውሉ የነበሩ ልብሶቿ ለክብር ሆኑ፤
ለዝሙት ይዘረጉ የነበሩ እጆች ለጽድቅ ተዘረጉ፤
ለዝሙት ይንበረከኩ የነበሩ እግሮቿ ለስግደት ተንበረከኩ፤
የጎልማሳ ቀልብን ሰብረው በመንገድ የሚያስቀሩ ዓይኖቿ የንስሓ እንባን አነቡ፤
ወደ ኃጢአት የእራት ግብዣ የሚገሰግሱ እግሮቿ ለክብር እንግድነት በቅድስና የእራት ግብዣ ቦታ ገሰገሱ፤
የጎልማሶች እጅ መንሻ በምትቀበልበት እጆቿ የተለየ ሽቱ ለነገሥታት እንደሚገባው ንጉሠ ነገሥት ለሆነው ለክርስቶስ አቀረበች፡፡
ይህች ዕለት ለእርሷ የተቀደሰ ሐሳብን ያሰበችበት፣ ያባከነችውን ጊዜ የምትክስበት፣ ለኃጢአት መኳኳል ትጠቀምበት የነበረውን ጊዜ ለጽድቅ ያደረገችበት ቅዱስ ዕለት፤ ከዓለም ሁካታና ጩኸት የተለየችበት ቅድስት እለት ናት፡፡
ዛሬ እኛ ከነበርንበት ውደቀት ለመውጣት ብዙ ምክንያች እንደረድራለን ያለንበትን ቦታና በዙሪያችን ያሉ ሰዎችን ከውደቀታችንም ላለመነሳት ምክንያት እናደርጋቸዋለን፡፡ ከዚህች ብርቱና ቆራጥ ሴት የምንማረው ለበጎ ተግባር ቁርጥ ውሳኔ መወሰንና ፈጥኖ በተግባር ማዋልን ነው። ያኔ ታላቅ የሕይወት ለውጥ በኑሯችን ይከሰታል።
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን

ሰሙነ ሕማማት ሠሉስ

ከመምህር ተፈሪ መንገሻ

በኢ.ኦ.ተ.ቤ/ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት የሰሙነ ሕማማት ዕለታት የየራሳቸው ስያሜና ምሥጢር አላቸው። ከእነዚያ መካከል ዕለተ ሠሉስ የትምህርት ቀን የጥያቄ ቀን በመባል ይታወቃል።

ይህንንም አስመልክቶ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በዕለቱ ጌታ ረጅም ትምህርት ያስተማረበትና ከአይሁድ፣ ከጸሓፍትና ከፈሪሳውያን ብዙ የተንኮል ጥያቄዎችን ተቀብሎ ለእነርሱም በጥበብ መልስ የሰጠበትን ድንቅ ትምህርት ሥርዓት ሠርታ ትዘክራለች/ታስታውሳለች። ይህች ዕለት የሰው ልጅ ውሱን በሆነው አዕምሮውና በተንኮል በተሞላው ልቡ ጥበብንና እውነትን (ክርስቶስን) ሊፈትን የሞከረበትና ጥበብ ክርስቶስ ግን ጥያቄአቸውን በጥያቄ የረታበት፣ ሐሰታቸውን የገለጠበት ዕለት ነው።

በሰኞ ዕለት ነጋዴዎችን ከቤተ መቅደሱ በማስወጣት ስላነጻ፣ ስለገሠጸ በማግሥቱ ማክሰኞ ዕለት ይህንን በማን ሥልጣን እንደሚያደርገውና ሌሎች ብዙ ጥያቄዎችን ጠይቀውታል። (ሉቃ. ፲፥፵፭)

በእነዚህ ጥያቄዎች ውስጥ ብዙ ጥልቅ ምሥጢራትን የያዘ ክፍል ነውና እነርሱን በዝርዝር ከፋፍለን እንደሚከተለው እንዳስሳቸዋለን።

ተንኮል በጥበብ ፊት (ሉቃ. ፳፥፩-፰)

በሰኞ ዕለት ጌታችን ቤተ መቅደሱን ከነጋዴዎች ማጽዳቱና የሃይማኖቱን ሥርዓት ወደ ንግድ የለወጡትን ማስወጣቱ (ሉቃ. ፲፱፥፵፭) በቤተ መቅደሱ ላይ የበላይነት አለን የሚሉት የካህናት አለቆችና ጸሐፍት በእነርሱ ዘንድ “የጥቅም መነካት” ፈጥሮባቸው ነበር።

በነጋታው በዕለተ ሠሉስ ጌታችን በቤተ መቅደስ እያስተማረና ወንጌልን እየሰበከ ሳለ፣ እነዚህ መሪዎች ከሽማግሌዎች ሆነው በመምጣት ድንገተኛ “የሥልጣን ጥያቄ” አቀረቡ።

“ወይቤልዎ፥ ንግረነ በመባሕተ መኑ ትገብር ዘንተ? ወመኑ አብሐከ ትግበር ከመዝ? ንገረን ይህንን በምን ሥልጣን ታደርጋለህ? ወይስ ይህን ሥልጣን የሰጠህ ማነው? አሉት” (ሉቃ. ፳፥፪)

ይህንንም ሲሉ የሥልጣኑን ምንጭ፣ “የማድረግ መብት” ወይም “ሕጋዊ ፈቃድ” ማለታቸው ነው። እነርሱ ጌታችንን የጠየቁት እንደ አምላክ ሳይሆን “እኛ ካልሾምንህ፣ እኛ ካልፈቀድንልህ ቤተ መቅደሱን የማጽዳት መብት ከየት አገኘህ?” የሚል ለአንድ ሰው የሚጠየቅ በዘመኑ ቋንቋ የቢሮክራሲ ጥያቄ ነው።

ክፋት ልባቸውን ስላሳወረው በዓይናቸው የሚመለከቷቸውን ተአምራት አይቶ ከማመን ይልቅ ከባለሥልጣን የፈቃድ ወረቀት ጠየቁት። ለስሕተታቸው እውነተኛ ማስረጃ ማቅረብ ስለማይችሉ ይህንን ስሕተታቸውን የገለጠባቸውን እውነት ከመቀበል ይልቅ መለኮታዊውን እውነት በሰዋዊ ሥርዓት ለመለካት ሞከሩ።

ዛሬም በሕይወታችን ውስጥ እውነትና ቅድስና ሲመጣ ቀድሞ የሚቃወመን የልባችን ክፋት ጥቅመኝነት ነው። ሀገራችንንና ዓለማችንን ብሎም ቤተ ክርስቲያናችንን እየፈተነ ያለው ከእውነት መንገድ ይልቅ በሐሰት የተገነባ ዝና፣ ስግብግብነትና ሆዳምነት ነው።

በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በኑሯችን የአንድን ሰው መንፈሳዊ ፍሬ ከመመልከት ይልቅ፣ “ከየት መጣ? ማን ፈቀደለት? የእኛ ወገን ነውን? በሚል ሥጋዊ ቅናት የእግዚአብሔርን ሥራ እንቃወማለን።

ጸሐፍት ይህ መንፈሳዊ ውድቀታቸው ሳያንስ እውነትን ለመሸፈን ያደረጉት ጥረት ይደንቃል። ይህ ጥያቄያቸው በተንኮል የተሞላና በሁለት አማራጮች መካከል አጣብቂኝ ውስጥ የሚከት ጥያቄ ነበር።

➜ ሥልጣኔ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ቢል፦ አንተ ራስህን አምላክ አድርገሀል ብለው ሊከስሱት ነው።

➜ ሥልጣኔ ከሰው ዘንድ ነው ቢል፦ “እንግዲህ ተራ ሰው ከሆንክ እንዲህ ያለውን ታላቅ ድርጊት የማድረግ መብት የለህም” ብለው በሕዝብ ፊት ሊከሱትና ሊያስሩት ዐቅደው ነበር።

ጌታችን ግን የእነርሱን ተንኮል ተረድቶ መልሱን በጥያቄ መለሰላቸው።

➜ “ጥምቀቱ ለዮሐንስ እምአይቴኑ ይእቲ እምሰማይኒ ወሚመ እምሰብእኑ፣ የዮሐንስ ጥምቀት ከሰማይ ነበረችን ወይስ ከሰው? አላቸው።” (ሉቃ. ፳፥፬)

ይህ የጌታ ጥያቄ ጠያቂዎችን በራሳቸው ጥያቄ ወጥመድ ውስጥ የሚከት ጥያቄ ነበር። ጌታ እነርሱ ሊያጠምዱበት ከዘረጉት ወጥመድ አልፎ እነርሱን በጥያቄ አጠመዳቸው። እነርሱ ባሰቡበት መንገድ አለመመለሱ ብቻ ሳይሆን እነርሱን አጣብቂኝ ውስጥ የሚከታቸው የመልስ ጥያቄ ሆነባቸው። ስለ እርሱ ማንነት በራሳቸው አንደበት እንዲመልሱ የሚያደርግ ጥያቄ ነበር።

ጌታችን ዮሐንስ መጥምቅን ጠቅሶ የጠየቃቸው ለምንድነው? ቢሉ

➜ ዮሐንስ መጥምቅ ስለ ክርስቶስ “እነሆ የእግዚአብሔር በግ” (ዮሐ.፩፥፳፱) ብሎ መስክሯልና ነው።

ስለዚህ እነርሱም “ከሰማይ ናት” ካልን፦ የዮሐንስን ምስክርነት መቀበልና በክርስቶስ ማመን ነበረባቸሁ ሊለን ነው። “ከሰው ናት” ካልን ደግሞ ሕዝቡ ዮሐንስን እንደነቢይ ስለሚያከብሩት ሕዝቡን በመፍራት በሁለት የአጣብቂኝ መልስ ውስጥ ገቡ።(ሉቃ. ፳፥፭-፮)

እግዚአብሔርን ብዙ ጊዜ “ለምን እንዲህ ሆነብኝ?” ብለን ስንጠይቅ፣ እርሱ ደግሞ “ቀድሞ የሰጠሁህን ጸጋ ምን አደረግከው?” ይለናል። (ማቴ.፳፭፥፲፭)

ጌታ እዚህ ጋር እያሳየን ያለው እውነትን ፍለጋ ወደ ውጭ ከመሄዳችን በፊት ወደ ውስጣችን እንድንመለከት ነው። ብዙ ጊዜ መልሱ እጃችን ላይ እያለ እኛ ግን እግዚአብሔርን “ሥልጣንህን አሳይ” እንለዋለን።

➜ በልባቸው ላይ ሐሰትን ያነገሡና እውነትን መቀበል የተሳናቸው ጸሐፍት ለጌታ ጥያቄ በቀጥታ ከመመለስ ይልቅ እውነቱን እያወቁ እንዳላወቁ ሆነው “መልሰውም፦ ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም አሉት።” (ሉቃ. ፳፥፯)

➜ “አናውቅም” የሚለው መልሳቸው በታሪክ ውስጥ እጅግ አሳፋሪ ውሸት ነው። እውነቱን ስለማያውቁ ሳይሆን ማወቅ ስለማይፈልጉ ነውና። “ከሰማይ ብንል….ከሰው ብንል….” እያሉ የሚያሰሉት ስለ እውነት ሳይሆን ስለ ጥቅማቸውና ስለ ደኅንነታቸው ነበር።

ዛሬም በዘመናችን “አናውቅም” ባዮች በዝተዋል። በሀገራችን፣ በቤ/ክ አገልግሎታችንና አጠቃላይ በማኅበራዊ ሕይወታችን እውነት ሲገለጥና ግፍ ሲሠራ እያየን፣ ጥቅማችን እንዳይነካ “አላየሁም፣ አልሰማሁም፣ አናውቅም” እንላለን።  “ብርሃን ወደ ዓለም መጣ፣ ሰዎች ግን ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ወደዱ” እንዲል ቅዱስ ዮሐንስ። (ዮሐ. ፫፥፲፱)

➜ “ኢየሱስም፦ እኔም በምን ሥልጣን እነዚህን እንዳደርግ አልነግራችሁም አላቸው።” (ሉቃ. ፳፥፰)

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህንን የጌታ መልስ ሲተረጉም ጌታ መልስ የከለከላቸው ሊቀበሉት ዝግጁ ስላልሆኑና ለእሪያ ዕንቁ ስለማይጣል መሆኑን ይናገራል። (ማቴ. ፯፥፮)

ሰው በልቡ ክፋትን፣ ቂምንና ተንኮልን ሸምቆ የሚጸልየው ጸሎት መልሱ ዝምታ ነው። “በልቤስ በደልን አይቼ ብሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር።” (መዝሙር ፷፯፥፲፰) በማለት ነቢዩ ዳዊት እንደተናገረ፡፡

ስለዚህ እኛም፡-

➜የእግዚአብሔርን ሥራ በራሳችን አእምሮ አንመዝን። “ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና” (፩ኛ ቆሮ.፩፥፳፭)

➜ ለእውነት ታማኝ እንሁን። እንደ ጸሐፍት በሰዎች ዘንድ የሚመጣብንን “ውግረት፣ ይሉኝታን፣ መገፋትና ሞትን ወዘተ ፈርተን እውነትን መካድ አይገባንም። እንደ ዳዊት “እስመ ለልየ አአምር ጌጋይየ ወኃጢአትየኒ ቅድሜየ ውእቱ በኵሉ ጊዜ፤ እኔ መተላለፌን (በደሌን) አውቃለሁና፥ ኃጢአቴም ሁልጊዜ በፊቴ ነውና።” (መዝ.፶፩፥፫) ብለን እውነት ሐሰትን እንዲያሸንፍ በፊቱ ለንስሐ መቅረብና ማልቀስ አለብን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር፤ ወለወላዲቱ ድንግል፤ ወለመስቀሉ ክቡር