“በበረከት የሚዘራ በበረከት ደግሞ ያጭዳል” (፪ተኛ ቆሮ. ፱፥፮)
“በበረከት የሚዘራ በበረከት ደግሞ ያጭዳል” (፪ተኛ ቆሮ. ፱፥፮)
ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምእመናን በላከላቸው በሁለተኛ ክታቡ መልእክቱን ሲልክላቸው የእነርሱን ሥነ ልቡና የሕይወት ዘይቤያቸውንና ማኅበራዊ ትስስራቸውን ስለሚያውቅ የነዳያኑ ህልውና ዋስትና እንዲያገኝ ማኅበርና ጽዋ ለነዳያን ምገባ ይውል ዘንድ ሲመክራቸውና መስጠት መዝራት እንደሆነ በማስረዳት ብዙ የዘራ ብዙ ያገኛል” የሚለውን መርሕ ይዞ በብዙ እንደሚሰበስቡ ለማስረዳት ይህንን መልእክት ላከላቸው።
- ዘር የተባለው መልካም ሥራ (ምጽዋት) ነው። (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፮-፲)
- ዘር ሲዘራ ዝናቡ ያሰቅቃል፤ ምጽዋት ሲሰጥ ስስት ያሰቅቃል።
ዘር የተባለ ምጽዋት በትጋት ከዘሩት በበጋ መንግሥተ ሰማይ እንደሚደሰቱ “እለ ይዘርዑ በአንብዕ ወበሐሤት የአርሩ፤ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ ወጾሩ ዘርዖሙ፤ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ ወጾሩ ከላስስቲሆሙ፤ በልቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይለቅማሉ፤ በሄዱ ጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ።” (መዝ. ፻፳፮፥፭) እንዲል ገበሬ የሌሊቱ ቍር፣ ዝናሙ፣ ጭቃው እነዚህ ሁሉ ምቾቱን እየነሡት ተቋቁሞ እህሉን ለቀጠና ብሎ ሳይሰስት በእምነት ወጥቶ እየተራበ እየተጠማ በእርሻው ላይ ይዘራል።
- ዘር ሲዘራ ቅንጣቷ ዘር ሠላሳ፣ ስሳና መቶ እንደሚሆን የሚታወቀው በእምነት ነው፤ ምጽዋት ሲሰጥ በሰማያዊ መዝገብ ማስቀመጥ እንደሆነ የሚታወቀው በእምነት ነው። (ማቴ. ፮፥፱)
“እንጀራህን በውኃ ፊት ላይ ጣለው፤ ከብዙ ቀን በኋላ ታገኘዋለህና።” (መክ. ፲፩፥፩) መተርጕማኑ በአንድምታ እንደሚከተለው ያስቀምጡታል።
በውኃ ውስጥ የጣሉት እንዳይታይ ሰውረኃ ሳታሳይ ስጥ። አንድም በውሀ ውስጥ የጣሉት እንዳይገኝ ከዚያ ከሰውየው ዋጋዬን አገኛለሁ ሳትል ስጥ። አንድም ከውኃ ዳር የዘራ ሰው እንዳያጣ ከእግዚአብሔር ዋጋዬን አጣለሁ ሳትል ስጥ አንድም … ውስተ ገጸ ሰማይ ይላል ምግብህን በከርሠ ርኁባን፤ በተራበ ሰው ሆድ፣ መጠጥህን በጕርዔ ጽሙዓን፤ በተጠማ ሰው ጕሮሮ፣ ልብስህን በዘባነ ሩቃን፤ ልብስህን በተራቆተ ሰው ጀርባ አኑር።
የዘሪውም ነገር ከዚህኛው በምሥጢር የሚገናኝበት ጊዜ አለ፤ ዘሪው ንፁሕ ዘሩ በእርሻው ሲዘራ በዝናም በራሰ መሬት እንደሚበሰብስ ያውቃል፤ በስብሶ እንደማይቀር እና ተነሥቶ ብዙ እንደሚያፈራ አምኖ በተስፋ ይዘራዋል።
ስለዚህ ገበሬ ሞቶ መነሣትን የሚያምን ሃይማነተኛ ነው። በስብሶ መብቀል ትንሣኤ ሙታንን የሚያስረዳን ዓይነተኛ ማስረጃ ነውና “እውነት እውነት እላችኋለሁ፣ የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፤ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች። (ዮሐ. ፲፪፥፳፬)
ዳግመኛ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ዳግመኛ ስለመነሣት በሚያስተምርበት በመጀመርያ መልእክቱ በዘር መስሎ “አንተ ሞኝ አንተ የምትዘራው ካልሞተ ሕያው አይሆንም፤ የምትዘራውም ስንዴ ቢሆን ከሌላም ዓይነት የአንዱ ቢሆን ቅንጣት ብቻ ነው እንጂ የምትዘራው የሚሆነውን አካል አይደለም” ብሎ ያስረዳቸዋል። (፩ቆሮ. ፲፭፥፴፮-፴፯)
ምጽዋትም ቢሆን ለጊዜው ስንሰጥ በውኃ እንደሟሟ እንጀራ “በከርሠ ርኁባን፤ በተራቡት ሰዎች ሆድ” እንጥለዋለን፤ እንደሚበሰብስ ዘር እንደሚበቅል አውቀን በእምነት እንዘራዋለን። ይህንንም መጽሐፍ” እስመ በብዙኅ መዋዕል ትረክቦ፤ በብዙ ዘመን ታገኘዋለህና” እያለ ከቶ እንደማይጠፋ ያሳስበናል። (መክ. ፲፩፥፩)
በውኃ የተጣለ እንጀራ እንደማይገኝ ያደረግነው በጎ ሥራ ከሰው ዘንድ ባይገኝ ከአምላክ ዘንድ በዝቶ ይገኛል። “ለዘሰአለከ ሀቦ፤ ለሚለምንህ ሁሉ ስጥ”፤ “ግበር ሠናየ ለኵሉ ወፈድፋደሰ ለሰብአ ሃይማኖት፤ ለሁሉም ሰው በጎ ሥራን አድርግ ይልቁንም ለሀይማኖት ሰው አድርግ” እንዲል ትርጓሜ፤ እርዳታችንን ለሚፈልጉ ሁሉ እንድንሰጥ መጽሐፉ “ሀብ መክፈልተከ ለ፯ቱ ወለ፰ቱ፤ ገንዘብህን ለሰባትም ለስምንትም ሰው ስጥ” ይላል (መክ. ፲፩፥፪) ፤ መተርጕማኑ ሲያብራሩት፡-
ለጥቂትም ለብዙም ስጥ፤ አንድም ለ፯ቱ ለሰባ ዘመን ይሆነኛል ያልኸውን ወለ፰ቱ ለሰማንያ ዘመን ይሆነኛል ያልኸውን ስጥ፤ አንድም ለ፯ቱ በሃይማኖት ለሚመስሉህ ለፍጹማን ምእመናን ወለ፰ቱ በሃይማኖት ለማይመስሉህ ስጥ፤ በሃይማኖት የማይመስሉ መጥተው ቢለምኑ መስጠት በሃይማኖት ለሚመስሉ ባሉበት ወስዶ መስጠት ይገባል።
አስቀድመን በሃይማኖት የሚዛመዱንን መርዳት እንደሚገባን ከዚያ በኋላ ለሰው ወገን በሰብእናው ልንረዳው እንደሚገባ ያስገነዝቡናል። “በተነ ለችግረኞችም ሰጠ” (መዝ. ፻፲፪፥፱) እንዲል አምላክ ያደለንን ጸጋ እኛም ለሌሎች ችሮታችንን ለሚፈልጉ ሁሉ መድረስ ይኖርብናል።
ተማሪ ምን ሊሰጥ ይችላል?
“ያለውን የሰጠ ንፉግ አይባልም” እንዲሉ አበው ተማሪዎች እንደመሆናችን መጠን መስጠት የምንችለው ጊዜያችን፣ ሐሳባችን፣ ጉልበታችን፣ ምክራችን፣ በጎ ልቡናችን ሊሆን ይችላል፤ እንጂ የግዴታ ገንዘብ ወይም ቁሳቁስ ላይሆን ይችላል። “ብርና ወርቅ የለኝም፤ ይህን ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሣና ተመላለስ አለው።” (ሐዋ. ፫፥፮) ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ ነዳዩ ከሚፈልገውና ሌሎች ከሚሰጡት የተሻለ ጸጋ አደለው። እኛም ከብርና ከቁስ የተሻለ አበርክቶ ልናበረክት ስለምንችል ለዚህ ራሳችንን ማዘጋጀት ብቻ ነው የሚጠበቅብን ማለት ነው። ይኸውም፡-
- ለቤተ ክርስቲያን የምናወጣው ዐሥራት ባይኖረን ገቢ የሚያስገኙ ቋሚም ሆነ ጊዜያዊ ሰብሎችን እያለማን ገቢ ማስገኘት ይቻላል።
- ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ ተማሪዎችን የነገረ ሃይማኖት ትምህርት በማስተማር ትውልድን በኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ቀርጾ በሥነ ምግባር አንጾ በሃይማኖት ማጽናት ይቻላል።
- በአስኳላ ትምህርታቸው እያገዝናቸው በትምህርታቸው ውጤታማ ሆነው የሀገር ተረካቢ ትውልድን መፍጠር ይቻላል።
- የተለያዩ ግንዛቤ፣ ዕውቀትና ክሂሎትን የሚያዳብሩ ሥልጠናዎችን ማሠልጠን ያስፈልጋል።
- እኩይ ተግባራት እንዲወገድ በማኅበረሰብ ዘንድ ግንዛቤ መፍጠር፣ ወጣቶችን በኦርቶዶክሳዊ ቤተሰብ አደራጅቶ ራሳቸውን ከሱስ ነጻ ሆነው ሃይማኖታቸውን ከመናፍቃን ጥቃት እንዲከላከሉ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ማስታጠቅ (ኤፌ. ፮፥፲፩) ሕፃናት ያለጥመት በሃይማኖት ቀጥ ብለው እንዲያድጉ ወተት የሆነውን ቃለ እግዚአብሔር እየጋቱ ማሳደግ (፩ኛቆሮ. ፫፥፪) እንዲሁም ከመጤ ባሕል መታደግ የሚያስችሉን መንገዶች መዘርጋት ይቻላል።
- ዘር የተባለው የእግዚአብሔር ቃል ነው። (ማቴ. ፲፫፥፲፱-፳፫)
“ዘእንበለ ምሳሌሰ ኢተናገሮሙ፤ ያለምሳሌ አልተናገራቸውም” እንዲል (ማቴ. ፲፫፥፴፬) ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘለዓለማዊ የሆነው ወንጌለ መንግሥቱን ለሁሉም ሰው በሚገባውና በተሰማራበት የሥራ ዘርፍ ሲያስተምር ለገበሬዎች በዘር መስሎ አስተምሯቸዋል።
በዚህም መሠረት “ዘር” የተባለው ቃለ ወንጌል ሲሆን “ዘሪ” የተባለው ደግሞ ጌታችን ነው። ጌታችን “ሑሩ ወመሀሩ ኵሎ አሕዛበ፤ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ” ብሎ እንደአዘዛቸው (ማቴ. ፳፰) ያስተማሩ ሐዋርያትና ከእነርሱ እግር ሥር ተተክተው ዘለዓለማዊው የክርስቶስን ሕያው ቃል ለፍጥረተ ዓለም የሚያስተምሩ ሁሉ “ዘሪ” የሚለውን ስም ያገኛሉ።
“ዘር”
- ምቹ የሆነ ታርሶ የለሰለሰ ለም የሆነ እርሻ ይፈልጋል፤ ይህ ከሆነ ሥር ይሰዳል፤ ይበቅላል።
- ወፎች እንዳይለቅሙት መጠበቅ ያስፈልጋል።
- የተዘራበት ማሳ ከአረም የጸዳ መሆን አለበት፤ አረም ከሌለ ሳይቀጭጭ ደኅና ሆኖ ያድጋል፤ ስለዚህ በየጊዜው ሊታረም ይገባዋል።
- ዋግ እና መሰል ተባዮች እንዳያበላሱጽ ጸረ ተባይ መድኀኒት መርጨት ይጠይቃል።
- የተዘራበት ማሳ በሰውም ሆነ በእንስሳ መረገጥ የለበትም በአጥር ቅጥር ሊከለል ይገባዋል።
በዚህ መልኩ መንከባከብ ከተቻለ ጥሩ ምርት መሰብሰብ ይቻላል።
እነዚህ የዘረዘርናቸው ተግባራት ሁሉ የሚሠራው ዘሪው ብቻ ላይሆን ይችላል፤ ሌሎች እነዚህን ተግባራት የሚፈጽም ግብረ ኀይል ይኖራል፤ እኛም በወንጌል ዘር ሱታፌያችን የየቅል ነው፤ ድርሻችን መዝራት ብቻ ላይሆን ይችላል፤ የሚዘራው ዘር ለፍሬ እንዲበቃ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን መሥራት ይጠበቅብናል።
ሁሉም ሰው ተመሳሳይ የሥራ ድርሻ ሊኖረው አይችልም፤ “የጸጋ ስጦታ ልዩ ልዩ ነው፤ መንፈስ ግን አንድ ነው” እንዲል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛቆሮ. ፲፪፥፬) ሁላችንም የተለያየ ስጦታ አለን።
ስለሆነም የተለያየ ስጦታችን ተጠቅመን አንድ ወንጌልን እንሰብካለን። “አሕዛብ አብረው እንዲወርሱ፣ በአንድ አካልም አብረው እንዲሆኑ፣ በወንጌልም መስበክ በክርስቶስ ኢየሱስ በሆነ የተስፋ ቃል አብረው እንዲካፈሉ …” (ኤፌ. ፫፥፭) እንዲል ሐዋርያው አማኝ ሁሉ በተረዳው ልክ ያንን የተረዳውን እውነት ለሌሎች የማጋራት ግዴታ አለበት። “ይሁን እንጂ፥ መጥቼ ባያችሁ ወይም ብርቅ በአንድ ልብ ስለ ወንጌል ሃይማኖት አብራችሁ እየተጋደላችሁ በአንድ መንፈስ እንድትቆሙ ስለ ኑሮአችሁ እሰማ ዘንድ ለክርስቶስ ወንጌል እንደሚገባ ኑሩ።” (ፊል. ፩፥፳፯) ይላል።
በመሆኑም ማንኛውም ሰው በወንጌል አገልግሎት “መክሊቴ ምንድነው?” የሚለውን መለየት ይኖርበታል። ሁሉም ሰው በስብከተ ወንጌል አገልግሎት የድርሻውን እንዲወጣ ኃላፊነት አለበት፣ ነገር ግን ይህንን አገልግሎት ለመተግበር የግድ ዐውደ ምሕረት ላይ ቆሞ መስበክ፣ መተርጎም፣ ለሰንበት ተማሪዎች ኮርስ መስጠት ላይጠበቅበት ይችላል። የግድ ሥልጣን ላይ መቀመጥ አይጠበቅበትም፤ ነገር ግን “ወንድሞች ሆይ ስለ እኔ ወደ እግዚአብሔር እየጸለያችሁ ከእኔ ጋር ትጋደሉ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስና በመንፈስ ፍቅር እለምናችኋለሁ፤” (ሮሜ ፲፭፥፴) ብሎ እንዳዘዘ ሐዋርያው መምህራንን መራዳት ታላቅ አገልግሎት ነው።
የሚማሩ ተማሪዎችን መቀስቀስ ማትጋትና የመማር ማስተማር ሁኔታዎችን ማመቻቸት፣ ጉባኤ እንዲዘጋጅ ማስተባበር፣ በተሰማራንበት ሁሉ ተተኪ እንዲኖር ሥልጠናዎች እንዲዘጋጁ ከሚመለከታቸው አጋር አካላት ጋር መቀናጀት ያስፈልጋል፤ እነ ፌቬን የቅዱስ ጳውሎስን ትምህርት ተደራሽ እንደሚያደርጉ የመምህራኑ ትምህርት ለምእመናን በተለያየ መንገድ ተደራሽ ማድረግ፣ የኢአማንያን ጥያቄ በመለየት አደራጅቶ በመምህራን ዘንድ ምላሽ በማሰጠት ትውልዱን ከስሑት አስተሳሰብ መጠበቅ ከቻልን የተዘራውን የክርስቶስ የመንግሥቱ ወንጌል ፍሬ እንዲያፈራ የድርሻችን መወጣት ችለናል።
ይህንን ለማድረግ የግቢ ጉባኤ ልጆች በክረምት ወደ ቤተሰብ ለዕረፍት ስትሄዱ በማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎት መስመር ላይ ሆናችሁ ዘር የክርስቶስ ወንጌል ሲዘራ የበኵላችሁን ተወጥታችሁ መከር ሲደርስ ከዘሪው ጋር ሐሴት ልታደርጉ ይገባል። “በእነርሱም መካከል የሕይወትን ቃል እያቀረባችሁ በዓለም እንደ ብርሃን ትታያላችሁ፤ ስለዚህም በከንቱ እንዳልሮጥሁ በከንቱም እንዳልደከምሁ በክርስቶስ ቀን የምመካበት ይሆንልኛል። … እናንተም ደግሞ እንዲሁ ደስ ይበላችሁ ከእኔም ጋር አብራችሁ ደስ ይበላችሁ።” (ፊሊ. ፪፥፲፮-፲፰) እንዲል ዛሬ ከእርሱ ጋር ከደከምን ነገ በመንግሥተ ሰማያት ከእርሱ ጋር ደስ ይለናል። ሁላችንም የምንሰበስበው በበተነው ልክ የምናጭደው በዘራነው መጠን መሆኑን ተረድተን ሳንታክት የወንጌልን አገልግሎት ለማስፋት መሮጥ አለብን።
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን።
አበበ ፍቅሬ
ይሁዳ እና የሰዎች ስሑት አረዳድ
ከዲ/ን ኃይለማርያም ታደሰ
“የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት፤ ያ ሰው ባልተወለደ ይሻለው ነበር አለ።” (ማቴ. ፳፮፥፳፬)
ውድ የእግዚኣብሔር ቤተሰቦች ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለሞት አሳልፎ ስለሰጠው ስለ አስቆሮቱ ይሁዳ የሚናገር ነው። ይህ ሰው ስሙ ከግብሩ ያልተባበረ ነው ይሁዳ ማለት ታማኝ ማለት ሲሆን፣ ግብሩ ግን ቆርሶ ላጎረሰው ቀዶ ላለበሰው ከነበደሉ ለተቀበለው አባቱና አምላኩ ያልታመነ ነው።
“የአስቆሮቱ” (Iscariot) የሚለው መጠሪያ ግን የተሰጠው ከትውልድ ቦታው በመነሣት ነው። “የአስቆሮት ሰው የሚሆን ያሲያዘው ይሁዳ” እንዲል ትርጓሜ ወንጌል (ማቴ. ፲፥፬) “የአስቆሮት ሰው የሚሆን ይሁዳ” (ማቴ. ፳፮፥፲፬) በዕብራይስጥ “ኢሽ–ኬርዮት” (Ish Kerioth) ማለት “የኬርዮት ሰው“ ማለት ነው። ኬርዮት በይሁዳ ምድር ደቡባዊ ክፍል የምትገኝ አንዲት ትንሽ ከተማ ናት፤ ይህም ሐጾር የምትባለውም ቂርያትሐጾር” ከተባለችው ከተማ ቂርያት የተገኘ ስም ነው። (ኢያሱ ፲፭፥፳፭) አባቱ “ስምዖን“ ይባላል። (ዮሐ. ፮፥፸፩፤ ፲፪፥፬፤ ፲፫፥፪፤ ፲፫፥፳፮)
በይሁዳ ዙሪያ የተነገሩ ትንቢቶች
በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ ስለ አስቆሮቱ ይሁዳ ማንነት፣ ክሕደት እና አምላካችን ስለተሸጠበት የብር መጠን በርካታ ትንቢቶች ተነግረዋል። ዋና ዋናዎቹ የትንቢት ክፍሎች እንደሚከተለው ቀርበዋል፦
- የማዕድ አጋር የመሆኑ ትንቢት
“የሰላሜ ሰው የታመንሁበት እንጀራዬን የበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣ።” (መዝ. ፵፩፥፱) ፍጻሜው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻው ራት ላይ ይህ ትንቢት በእርሱ ላይ እንደሚፈጸም ሲናገር፦ “ነገር ግን መጽሐፍ፦ እንጀራዬን የሚበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣብኝ ያለው ይፈጸም ዘንድ ነው።” ብሏል። (ዮሐ. ፲፫፥፲፰) ለጊዜው ንጉሥ ዳዊትን ከድቶ ከአቤሴሎም ጋር ለተሰለፈው ለአኪጦፌል የተነገረ ሲሆን፤ ፍጻሜው ግን የዳዊት ልጅ የተባለው ክርስቶስን ለከዳው ለይሁዳ ነው።
- ጌታውን በሠላሳ ብር የመሸጡ ትንቢት
ነቢዩ ዘካርያስ አስቀድሞ “እኔም፦ ደስ ብሏችሁ እንደ ሆነ ዋጋዬን ስጡኝ፤ ያለዚያ ግን ተዉት አልሁ። እነርሱም ለዋጋዬ ሠላሳ ብር መዘኑ። እግዚአብሔርም፦ የተስማሙበትን የከበረውን ዋጋዬን በግምጃ ቤቱ ውስጥ አኑረው አለኝ። እኔም ሠላሳውን ብር ወስጄ በእግዚአብሔር ቤት ባለው በግምጃ ቤቱ ውስጥ አኖርሁት።” በማለት ተናግሯል። (ዘካ. ፲፩፥፲፪-፲፫) ይሁዳ ጌታን አሳልፎ ለመስጠት ከካህናት አለቆች ጋር የተስማማበትና በኋላም የተጸጸተ መስሎ ብሩን በቤተ መቅደስ የጣለበት ክፍል ነው። (ማቴ. ፳፮፥፲፭፤ ፳፯፥፫-፭)። በዚህ የወንጌል ክፍል ላይ ይህ ትንቢት በኤርምያስ እንደተነገረ “በዚያን ጊዜ በነቢዩ በኤርምያስ የተባለው፦ ከእስራኤል ልጆችም አንዳንዶቹ የገመቱትን፥ የተገመተውን ዋጋ ሠላሳ ብር ያዙ። ጌታም እንዳዘዘኝ ስለ ሸክላ ሠሪ መሬት ሰጡት የሚል ተፈጸመ።” እያለ ወንጌላዊው ማቴዎስ ይነግረናል። (ማቴ. ፳፯፥፱) የአንድምታ ሊቃውንት ይህንን ሲያብራሩት ኤርምያስ የመሬቱን መገዛት ተንብዮ ነበር።(ኤር. ፴፪፥፲፬) ዘካርያስ ደግሞ የብሩን መጠን ተናግሯል፤ ማቴዎስ ግን የሁለቱንም ትንቢት በአንድ ላይ አጠቃሎ በዋናው ነቢይ በኤርምያስ ስም ጠራው በማለት ያስታርቁታል።
- የሸክላ ሠሪው መሬት ትንቢት
“ሂድ፥ ከሸክላ ሠሪ ገምቦ ግዛ… “ (ኤር. ፲፱፥፩-፲፩፤ ኤር. ፴፪፥፮-፱) የካህናት አለቆች የደሙን ዋጋ (፴ውን ብር) ተቀብለው ለባዕድ አገር ሰዎች መቃብር የሚሆን የሸክላ ሠሪውን መሬት ገዙበት፤ ያም መሬት እስከዛሬ “የደም መሬት” (አኬልዳማ) ይባላል። (ማቴ. ፳፯፥፯-፰)
- የሐዋርያነት ሥልጣኑ በሌላ ስለመተካቱ
“ዘመኖቹም ጥቂት ይሁኑ፤ ሹመቱንም ሌላ ይውሰድ። (መዝ. ፩፻፱፥፰) የትንቢቱን ፍጻሜ ደግሞ ጌታ ካረገ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ በሐዋርያት መካከል ቆሞ የዳዊትን ትንቢት ጠቅሶ በይሁዳ ምትክ ማትያስን በመምረጥ ተፈጽሟል። (ሐዋ. ፩፥፲፮-፳) «ሹመቱን ሌላ ይውሰዳት» ማለት ይሁዳ ከ፲፪ቱ የሐዋርያት ቁጥርና ክብር ወጥቶ በቦታው ቅዱስ ማትያስ መተካቱን ያሳያል።
ሀ. የይሁዳ ኢየሱስ ክርስቶስን አሳልፎ መስጠትና የክርስቶስ ስቅለት
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሐዲስ ኪዳን አንድምታ ትርጓሜ እና በሊቃውንት ትምህርት መሠረት ይሁዳ ክርስቶስን አሳልፎ ባይሰጠውም እንኳ የክርስቶስ ስቅለትና ሞት አይቀርም ነበር። ሊቃውንቱ ለዚህ የሚሰጡት ዝርዝር ምሥጢራዊ ማብራሪያ እንደሚከተለው ይቀርባል፦
- ስቅለቱ የእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ዕቅድ መሆኑ
የክርስቶስ ሰውን የማዳን ተግባር ዓለም ሳይፈጠር አስቀድሞ በልበ ሥላሴ ይታወቃል። “እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውሃ ፈሳሽ” በድንገት በይሁዳ ክሕደት ምክንያት የተፈጠረ ክስተት አይደለም። ቅዱስ መጽሐፍ ”ዓለም ሳይፈጠር እንኳ አስቀድሞ ታወቀ፤ ነገር ግን እምነታችሁና ተስፋችሁ በእግዚአብሔር ይሆን ዘንድ ከሙታን ባስነሣው ክብርንም በሰጠው በእግዚአብሔር በእርሱ ስለምታምኑ ስለ እናንተ በዘመኑ መጨረሻ ተገለጠ።” (፩ኛ ጴጥ. ፩፥፳-፳፩) “ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል” እንዲል ክርስቶስ ዓለም ሳይፈጠር የታረደው ተብሏል። (ራእይ ፲፫፥፰)
እርሱንም በእግዚአብሔር በተወሰነው ሐሳቡና በቀደመው ዕውቀቱ ተሰጥቶ በዓመፀኞች እጅ ሰቅላችሁ ገደላችሁት። (ሐዋ. ፪፥፳፫)የአንድምታ ማብራሪያው “ክርስቶስ የሞተው በእግዚአብሔር በታወቀው ሐሳቡና በወሰነው ፈቃዱ ነው፤ ማለትም እግዚአብሔር ወዶ መክሮ ባደረገው ሥጋዌ እንዳያችሁት መጠን ወይም (ቅድምናውን ሥጋዌውን እንዳያችሁት መጠን) ለኃጥኣን አሳልፋችሁ ሰጣችሁት፤ ሰቅላችሁ ገደላችሁት።“ ይላል። ስለዚህ አምላክ ለሰው የሰጠው የነጻነት ፈቃድና የሰውን ልጅ የማዳን ዘለዓለማዊ ዕቅድ በሰዎች ክፋት ወይም በይሁዳ ታማኝ መሆን አለመሆን አይወሰንም።
- ይሁዳ ባይኖርም አይሁድ ጌታን ለመያዝ ይፈልጉ ነበር።
አይሁድና የካህናት አለቆች ይሁዳ ወደ እነርሱ ከመምጣቱ በፊትም እንኳ ጌታን ለመግደልና ለመስቀል በተደጋጋሚ ይመክሩ ነበር። ክርስቶስን የመግደል ሐሳብ በአይሁድ ለሦስት ዓመት ያህል የታሰበ ዕቅድ ነበር፤ ይሁዳ የመጣው አይሁድ መክረው ከጨረሱ በኋላ ነው። “ሕዝቡም ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለ ሕዝቡ ይሞት ዘንድ እንዲሻለን አታስቡም አላቸው። ይህንም የተናገረ ከራሱ አይደለም፤ ነገር ግን በዚያች ዓመት ሊቀ ካህናት ነበረና ኢየሱስ ስለ ሕዝቡ ሊሞት እንዳለው ትንቢት ተናገረ፤ ስለ ሕዝቡም ሁሉ አይደለም፥ ነገር ግን የተበተኑትን የእግዚአብሔርን ልጆች ደግሞ በአንድነት እንዲሰበስባቸው ነው እንጂ። እንግዲህ ከዚያ ቀን ጀምረው ሊገድሉት ተማከሩ“ (ዮሐ. ፲፩፥፶-፶፫)
“ከሁለት ቀን በኋላ ፋሲካ እንዲሆን ታውቃላችሁ፤ የሰው ልጅም ሊሰቀል አልፎ ይሰጣል አለ። በዚያን ጊዜ የካህናት አለቆች የሕዝብም ሽማግሎች ቀያፋ በሚባለው በሊቀ ካህናቱ ግቢ ተሰበሰቡ፤ ኢየሱስንም በተንኰል ሊያስይዙት ሊገድሉትም ተማከሩ፤ ነገር ግን፦ በሕዝቡ ዘንድ ሁከት እንዳይነሣ በበዓል አይሁን አሉ።” (ማቴ. ፳፮፥፪-፭)
የይሁዳ ሚና ምን ነበር? ይሁዳ ያደረገው ነገር ቢኖር አይሁድ በሕዝቡ ረብሻ እንዳይነሣ በመፍራት ሕዝብ በሌለበት በምሽት በጌቴሴማኒ የአትክልት ሥፍራ ለይቶ ማሳየት ብቻ ነበር። ይሁዳ ባይኖር ኖሮ አይሁድ በሌላ መንገድ ወይም በሌላ መሪ መያዛቸውና መስቀላቸው አይቀርም ነበር።
- የይሁዳ ክሕደት “ምክንያት” እንጂ “አስገዳጅ” አልነበረም (Foreknowledge vs Predestination)
ይሁዳ ክርስቶስን አሳልፎ እንደሚሰጥ ትንቢት ተነግሯል። (መዝ. ፵፩፥፱) ይሁዳን ወስኖበት አይደለም። እግዚአብሔር በዘላለማዊ ዕውቀቱ (Foreknowledge) ይሁዳ በገዛ ነጻ ፈቃዱ የሚያደርገውን ክፋት አስቀድሞ በነቢያት ተናገረ እንጂ፣ አንዳንዶች እንደሚሉትይሁዳ ለዓለም መዳን የተሠዋ “መሥዋዕት” ወይም “አጋዥ” አይደለም።
ጌታችን ራሱ በወንጌል የተናገረው ቃል “የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት፤ ያ ሰው ባልተወለደ ይሻለው ነበር ።” (ማቴ. ፳፮፥፳፬) የአንድምታው ምሥጢር ደግሞ “ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል” ማለት ስቅለቱና ሞቱ የአምላክ ፈቃድና የትንቢት ፍጻሜ ስለሆነ አይቀርም ማለት ሲሆን፣ “ለዚያ ሰው ወዮለት” ማለቱ ግን ይሁዳ ወደ ክሕደት መግባቱ በገዛ ክፉ ፈቃዱና በስግብግብነቱ ምክንያት በመሆኑ ለፍርዱ ተጠያቂ መሆኑን ያሳያል።
ታላቁ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው ላይ ይህንን ምሥጢር ሲያጠቃልለው እንዲህ ብሏል፦ «ይሁዳ ክርስቶስን አሳልፎ ባይሰጠው ኖሮ ክርስቶስ አይሰቀልም ነበርን? በፍጹም ይሰቀል ነበር! እርሱ የመጣው ለዚህ ነውና። ይሁዳ ጌታን አሳልፎ የሰጠው የሰውን ልጅ ለማዳን አስቦ ሳይሆን በገንዘብ ፍቅር ተገፋፍቶ ነው። እግዚአብሔር ግን የይሁዳን ክፋት ለዓለም ድኅነት መገኛነት ተጠቀመበት። ይሁዳ ባይከዳ ኖሮ የክርስቶስ ስቅለት በሌላ መንገድ ይፈጸም ነበር፤ ይሁዳ ግን ከሐዋርያነት ክብር ሳይወጣ በታማኝነት ይኖር ነበር» Homily 81: On Matthew 26:24)
- የአምላክ ፍጹም ትሕትና እና ትዕግሥት
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይሁዳ እንደሚከዳው አስቀድሞ እያወቀ፣ በመጨረሻው ራት ላይ እግሩን አጥቦታል፤ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙንም ሰጠው። (ዮሐ. ፲፭፥፭) የወንጌል አንድምታ “ጌታ የይሁዳን እግር ያጠበው፣ እርሱ በገዛ ፈቃዱ ለጥፋት ቢሮጥም አምላክ ግን እስከ መጨረሻዋ ሰዓት ድረስ የፍቅርና የንስሓ ዕድል እንዳልነፈገው ለማሳየት ነው።” ይላል።
- የክርስቶስ ሞት የፍቅር መሥዋዕትነት እንጂ የግዴታ አለመሆኑ
በነገረ መስቀል ትምህርት ክርስቶስ የሞተው በፈቃዱ እንጂ በይሁዳና በአይሁድ አስገዳጅነት አይደለም። (ዮሐ. ፲፥፲፰) ይሁዳ ጌታን አሳልፎ በሰጠበት በጌቴሴማኒ «እኔ ነኝ» ባለው ጊዜ ወታደሮቹ ወደ ኋላ አፈግፍገው መሬት ላይ ወድቀዋል። (ዮሐ. ፲፰፥፮) ሊቃውንት ይህንን ሲተረጉሙ፦ “በአንድ ቃሉ መሬት የጣላቸው አምላክ፣ ሊይዙት የቻሉት ለዓለም ድኅነት ሲል ራሱን ዝቅ አድርጎ ስለሰጣቸው ብቻ እንደሆነ ለማሳየት ነው።” ይላሉ።
- ይሁዳ የመኮነኑ ምክንያት መካዱ ብቻ ሳይሆን ተስፋ መቁረጡ ነው።
በነገረ ድኅነት ትምህርት በመስቀል ላይ የፈሰሰው የክርስቶስ ደም የዓለምን ኃጢአት ሁሉ ያስተሠርያል። (፩ኛ ዮሐ. ፩፥፯) ይሁዳ ራሱን ከማጥፋቱ በፊት ወደ ቀራንዮ መስቀል ሥር ሄዶ ቢሆን ኖሮ የመስቀሉ ደም እርሱንም ያድነው ነበር። የይሁዳ ትልቁ ስሕተት ኃጢአቱ ከክርስቶስ የማዳን ኃይል አስበልጦ ተስፋ በመቁረጡ ነው።
ለ. የአስቆርቱ ይሁዳ አሟሟት
የአስቆሮቱ ይሁዳ አሟሟትን በተመለከተ የተጻፉት ክፍሎች፣ መጽሐፍ ቅዱስን ያለ ምሥጢር መረዳት ለሚያነቡ ሰዎች እርስ በእርሳቸው እጅግ የሚጋጩ ከሚመስሉ ታሪኮች መካከል ዋነኛው ነው። በመጀመሪያ ሁለቱ የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ታሪኩን የመዘገቡበትን መንገድና ግጭት የሚመስለውን ነጥብ ስንመለከት “ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሄደና ታንቆ ሞተ።”ይላል። (ማቴ. ፳፯፥፭) ካህናቱም በገንዘቡ የመቃብር ቦታ እንደገዙበት ይናገራል።
በሌላኛው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ደግሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ስለ ይሁዳ ሲናገር “ይህም ሰው በዓመፅ ዋጋ መሬት ገዛ በግንባሩም ተደፍቶ ከመካከሉ ተሰነጠቀ አንጀቱም ሁሉ ተዘረገፈ”ይላል። (ሐዋ. ፩፥፲፰ ) ከዚህ ጋር ተያይዞ የአንድምታ መጽሐፍ ይሁዳ የሞተው በጌታ ዕርገት ሰዓት ነው ይላል።
ጥያቄው፦ ይሁዳ የሞተው ታንቆ ነው ወይስ በግንባሩ ተደፍቶ ተሰንጥቆ? መሬቱንስ የገዛው ይሁዳ ራሱ ነው ወይስ የካህናት አለቆቹ? የሞተው በታነቀ ጊዜ ወይስ በዕርገት የሚለው ነው።
በመጽሐፍ ቅዱስ በተለያየ አገላለጽ ተዘግቦ ስናየው የሚጋጭ ቢመስልም ሊቃውንት ያቀኑታል፤ የአንድምታ ሊቃውንት የማቴዎስ ወንጌል አንድምታ (ማቴ ፳፯፥፭) እና የሐዋርያት ሥራ አንድምታ (ሐዋ ፩፥፲፰) ላይ ይህንን ታሪክ ፍጹም በሚስማማ መንገድ በሚከተሉት ሦስት ታላላቅ ምሥጢራት ያብራሩታል፦
- የአሟሟቱ ቅደም ተከተል
አይሁድ ጌታን እንይዛለን ሲሉ በተአምር ሲያመልጣቸው ያይ ስለነበር እሱም እንደልማዱ በተአምር ያመልጣል እኔም ወርቄን እንደያዝሁ እቀራለሁ ብሎ ሠላሳ ብር ተቀብሎ አሳልፎ ሰጣቸው። ጊዜው ደርሶ ይሞት ዘንድ እንደተፈረደበት ባየ ጊዜ ጻድቅ ሰው አስገደልኩ፣ ንጹሕ ደም አስፈሰስኩ ብሎ ሠላሳውን ብር ይዞ ተቀበሉኝ አላቸው።
አይሁድም አንድ ጊዜ የወደድከውን ሰጥተንሀል፤ የወደድነውን ሰጥተኸናል፤ አንተ ከእኛ፣ እኛ ከአንተ ምንም የለን ለራስህ ዕወቅ አሉት። በዚህ ጊዜ ይሁዳ ጌታን አሳልፎ በመስጠቱ ከፍተኛ ጸጸትና ተስፋ መቁረጥ ውስጥ ገባ። ጌታችን በፈቃዱ ለሞት መሰጠቱንና በተአምር እንደማያመልጥ ባወቀ ጊዜ፣ ይሁዳ በልቡ እንዲህ ሲል አሰበ፦ “ጌታአሁን ይሞታል፤ እርሱ ወደ ሲዖል ወርዶ እዚያ ያሉትን ነፍሳት በሙሉ ሊያወጣቸው ነው። ስለዚህ እኔ ቀድሜ ልሙትና ሲዖል ልጠብቀው፤ ሲመጣ እኔንም አብሮ ያወጣኛል” በዚህ የተሳሳተ ሐሳብ ተገፋፍቶ ሄዶ በገመድ ዛፍ ላይ ታነቀ።
ይሁዳ ሊታነቅባት የሞከራት ያቺ ዛፍ (በትውፊት የበለስ ዛፍ ናት) በተአምር ቁልቁል እያጎነበሰችና ወደ ላይ እየተነሣች “ንስሓ ግባ እንጂ አትሙት” እያለች ለ፯ ሰዓታት ያህል መከረችው። ይሁዳ ግን ንስሓ መግባትን እምቢ ስላለ በመጨረሻም ቀትር ላይ ከዛፏ ላይ ሲንጠለጠል ገመዱ ተበጥሶ ወደ መሬት ወደቀ። (አንድምታ ትርጓሜ ዘግብረ ሐዋርያት ፩፥፲፰)
- መሬት ላይ መውደቁና በሕመም መቆየቱ
ይሁዳ ከዛፉ ላይ ሲወድቅ ሆዱ ተቀዶ አንጀቱ ተዘረገፈ። ዕለቱን ግን አልሞተም። ይልቁንም በጽኑ ቁስልና ሕመም ተመቶ፣ አንጀቱ ተዘርግፎ ሳለ ነጋድያን ሲያልፉ አይተው “ለዘመዶቹ ያ ክፉ ሰው ወድቆ ይንፈራገጣል” ብለው ነግረዋቸውል። አንጀቱ ተሸክፎ (ታስሮ) ወደ ቤቱ ተወሰደ።
- የጌታ ማረግ እና የይሁዳ ፍጻሜ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምድራዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ በ፵ኛው ቀን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ወደ ሰማይ ማረጉ (መውጣቱ) በኢየሩሳሌም ከተማ ታላቅ ዜና ተሰማ። ይሁዳ በቤቱ በቁስል ተኝቶ ሳለ፣ የቤቱ ሰዎችና በዙሪያው የነበሩት ሁሉ እየሮጡ መጥተው “ያ የሸጥከው የናዝሬቱ ኢየሱስ እነሆ ዛሬ በታላቅ ክብርና በደመና ወደ ሰማይ ዐረገ (ወጣ)!” አሉት።
ይሁዳ ይህንን ታላቅ የምሥራች ሲሰማ፣ ጌታ ወደ ሲዖል ወርዶ ነፍሳትን ሲያወጣ “እኔንም ያወጣኛል” ብሎ አስቦ የነበረው ሐሳብ በሙሉ እንደከሸፈና እርሱ ግን በምድር ላይ ተለይቶ እንደቀረ ባየ ጊዜ በከፍተኛ ድንጋጤ፣ ጸጸትና ፍርሃት ተውጦ ከአልጋው ላይ ተነሥቶ ለማየት ሊወጣ ሲል፣ የቤቱ መቃን (የበሩ መወርወሪያ) በኃይል መታው። አንድም አያለሁ ብሎ ሲወጣ መላእክት የእሳት ጦር ይዘው ታዩት። ወደ አልጋ እሸሻለሁ ሲል የአልጋው ጫፍ ጎኑን ቀደደው። በዚያ ቅጽበት የታሰረው ሆዱ ተቀዶ፣ የቀረው አንጀቱ በሙሉ ተዘርግፎ፣ በግንባሩ ተደፍቶ በዚያው በዕለተ ዕርገት ፍጹም ክፉ አሟሟትን ሞተ።
ስለዚህ ማቴዎስ ይሁዳ ራሱን ያጠፋበትን የመጀመሪያውን ምክንያት (መታነቁን) ሲመዘግብ፤ ጴጥሮስ ደግሞ ከዛፍ ላይ ወድቆ መሬት ላይ መፈጥፈጡን እንዲሁም በሥጋው ላይ የደረሰበትን የአንጀት መጎልጎል መዝግቦታል። ሊቃውንት ደግሞ አስከሬኑ የደረሰበትን የመጨረሻውን(መሰነጣጠቁን) እና አሳልፎ የሰጠው አምላክ ወደ ሰማይ ማረጉን አመሥጥረው አስተማሩን።
ለ. መሬቱን ማን ገዛው? (በይሁዳ ስም መገዛቱ)
ወንጌላዊው ማቴዎስ መሬቱን የገዙት የካህናት አለቆች እንደሆኑ ይናገራል። ምክንያቱም የደም ዋጋ ስለነበረ ወደ መቅደስ ግምጃ ቤት ሊያስገቡት አልፈቀዱም። (ማቴ. ፳፯፥፯) ቅዱስ ጴጥሮስ ግን “ይህም ሰው በዓመፅ ዋጋ መሬት” ይላል። ሊቃውንቱ በአንድምታው ሲተረጉሙት መሬቱ የተገዛው በይሁዳ ገንዘብ እና በይሁዳ ስም ስለነበረ፣ በሕግና በታሪክ ደረጃ መሬቱን እንደገዛው ተቆጥሮበታል ማለት ነው። ልክ አንድ ሰው በገንዘቡ ሌላ ሰው ሄዶ መሬት ቢገዛለት፣ “እገሌ መሬት ገዛ” እንደሚባለው ሁሉ።
እንዳጠቃላይ በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ አስቀድሞ ማወቅ እንጂ አስቀድሞ መወሰን የሚባል አስተምህሮ የለም። “አስቀድሞ መወሰን ፤ predestination” ትምህርት የኦግስቲን የግል ፍልስፍናዊ እምነቱ ነው። ለሰው ልጅ እግዚአብሔር ነጻ ፈቃድ ሲሰጠው “ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና።” ብሎ የመብላትም አለመብላትም ሙሉ መብት ሰጠው፤ ይህ ሲባል ግን ትእዛዙን ሽሮ እንደሚበላ በመለኮታዊ ዕውቀቱ ያውቅ ነበር።
“አቅረብኩ ለከ እሳተ ወማየ ደይ እዴከ ኀበዘፈቀድከ፤ እሳትና ውሃ አስቀምጬልሃለሁ እጅህን ወደፈቀድከው ስደድ” ሲል ለሰው ልጅ በጎ የመሆን ክፉ የመሆን ነጻ ፈቃድ ተሰጥቶታል፤ “እምቅድመ ይፍጥሮ ለሰብእ የአምር ግብሮ፤ ሰውን ሳይፈጥረው በፊት ሥራውን ያውቃል” እንዲል ማናችንም ክፉ ወይ በጎ እንደምንሆን ሳንፈጠር ያውቀናል። ያውቀናል ማለት ግን ያስገድደናል ማለት አይደለም። ከክፋታችን ብንመለስ ዕድሜ እንደሚጨመርልን የሕዝቅያስ ታሪክ ያስገነዝበናል። (ሕዝ. ፳፥፩-፭)
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!
ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል
ከመምህር ተስፋሚካኤል ታደለ
በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ እና በመጻሕፍት ውስጥ የሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል አገልግሎትና አማላጅነት በብዙ ቦታዎች ላይ ተገልጿል። «ዑራኤል» የሚለው ስም ትርጉሙ «ብርሃነ እግዚአብሔር፣ የእግዚአብሔር ብርሃን” ማለት ሲሆን፣ እርሱ በብርሃናት ሁሉ ላይ የተሾመ፣ የፍርሃትና የረዓድ መጽናኛ እንዲሁም የእግዚአብሔርን ጥበብና ምሥጢር ለወዳጆቹ የሚገልጥ ታላቅ መልአክ ነው።
ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል በሥነ ፍጥረት ሕግጋትና በሰማያዊ ብርሃናት ዑደት ላይ የሠለጠነ መልአክ ነው። በመጽሐፈ ሔኖክ (በተለይም ከምዕራፍ ፳፩ እስከ ፳፭ ባሉት ክፍሎች) እንደተገለጸው፣ ቅዱስ ዑራኤል «በብርሃናት ላይ ሁሉ የተሾመ» (ሄኖክ ፮፥፪) እና የሰማይ አካላት ያለ አንዳች መዛነፍ በፈጣሪ በተሰጣቸው ሥርዓት መሠረት እንዲጓዙ የሚመራ ነው።
ነቢዩ ሄኖክ በመልአኩ ቅዱስ ዑራኤል መሪነት የሰማያትን ሥርዓት፣ የፀሐይንና የጨረቃን ጉዞ፣ የከዋክብት መውጫና መግቢያ መስኮቶችን እንዲሁም በምድር ላይ የሚነፍሱትን ፲፪ የነፋሳት ዓይነቶች ተመልክቷል። የሰማይ ብርሃናት በየሥልጣናቸው፣ በየዘመናቸውና በየመውጫቸው በሚመላለሱበት ጊዜ ሁሉ የመልአኩ ጥበቃና መሪነት አይለያቸውም።
ጨረቃ ብርሃኗን ከፀሐይ እየተቀበለች በየወሩ በመስኮቷ እየወጣችና እየገባች ጊዜያትንና ወራትን እንድትቆጥር፣ ከዋክብትም በየስሞቻቸውና በየክፍላቸው ተመድበው እንዲወጡ ለሔኖክ ያስጎበኘውና ምሥጢሩን ያሳወቀው ቅዱስ ዑራኤል ነው። በተጨማሪም በምድር ላይ ከሚነፍሱት ፲፪ የነፋሳት መስኮቶች መካከል አራቱ የበረከትና የሰላም ነፋሳት ምድርን የሚያለመልሙ ሲሆኑ፣ ስምንቱ የመቅሰፍት ነፋሳት ደግሞ ድርቅንና ጥፋትን የሚያመጡ ተፈጥሮአዊ ሂደቶች ናቸው። (መቅድመ ወንጌል) እነዚህ ሁሉ የተፈጥሮ ሕግጋት በፈጣሪ ፈቃድና በመልአኩ አስጎብኚነት የሚከናወኑ የሥነ-ፍጥረት ምሥጢራት ናቸው። ቅዱስ ዳዊት «ሰማያት የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ፤ የሰማይም ጠፈር የእጁን ሥራ ያወራል» (መዝ. ፲፱፥፩) እንዲል፣ ቅዱስ ዑራኤል የዚህን መለኮታዊ ሥርዓት ታላቅነት ለፍጥረታት የሚገልጥ መልአክ ነው።
ቅዱስ ዑራኤል በቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት «ከሣቴ ምሥጢር፤ ምሥጢር ገላጭ በመባል ይታወቃል። የተሰወረውን ምሥጢር መግለጥና በአዲስ ቋንቋ ማናገር የመንፈስ ቅዱስ ሀብት ቢሆንም፣ እግዚአብሔር ለቅዱስ ዑራኤል በወደዱትና እንዲያውቁ በተፈቀደላቸው ሰዎች አእምሮ ላይ ጥበብንና እውቀትን የማፍሰስ ጸጋ ሰጥቶታል። ለዚህም ዋናው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ ለዕዝራ ሱቱዔል የተደረገለት ታላቅ ተአምር ነው። «መልአኩ ዑራኤል አፍህን ክፈት፤ እኔም የማጠጣህን ጠጣ አለኝ… ብሎ አእምሮ ለብዎውን ገልጦለታል።» (ዕዝራ ፲፫፥፴፰)
ዕዝራ ለረጅም ወራት እግዚአብሔርን ደጅ ሲጠና፣ እግዚአብሔር ቅዱስ ዑራኤልን ልኮ የጥበብና የዕውቀት ጽዋ አጠጥቶታል፤ በዚህም ምክንያት የሰማዩን ምሥጢር ዐውቋል፣ የነገሩትን የማይረሳ አእምሮም አግኝቷል። በተመሳሳይ መልኩ ለነቢዩ ሔኖክ ምሥጢረ ሰማይንና ዕውቀትን ሁሉ የገለጠለት እርሱ እንደሆነ በመጽሐፈ ሄኖክ የተጻፈ ሲሆን (ሔኖክ ፳፰፣፲፫) ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም ልቡናውን ያበራለትና ድንቅ ድንቅ የድርሰትና የምሥጢር ቃላትን ያደለው ይህ መልአክ እንደሆነ በገድሉ ላይ ተመዝግቧል። አፋቸውን ከፍተው የምስጋና ቃል ለሚናገሩና እግዚአብሔርን ደጅ ለሚጠኑ ሁሉ ቅዱስ ዑራኤል አእምሯቸውን ያበራል፣ ጥበብን ያሳድራል፣ ከመከራ ሥጋና ከመከራ ነፍስም ይጠብቃቸዋል።
ቅዱስ ዑራኤል በሰው ልጅ የድኅነት ታሪክ ውስጥ ቀጥተኛ ተሳታፊ በመሆን ድንቅ አገልግሎት አድርጓል። ነቢዩ ዳዊት «የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሠፍራል፥ ያድናቸውማል» (መዝ. ፴፫፥፯) እንደተናገረው እግዚአብሔርን ለሚፈሩ ሰዎች በጭንቀት ጊዜ በመካከላቸው እየተገኘ ያጽናናቸዋል፣ ረዓድና ፍርሃት ላለባቸውም ታላቅ ረዳታቸው ነው። የመልአኩ ተራዳኢነት አገልግሎት በሚከተሉት ታላላቅ ታሪካዊ ክስተቶች ይገለጻል፦
● የክርስቶስን ደም በጽዋዕ መቀበል፦ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀራንዮ አደባባይ ደሙን በፈቃዱ ሲያፈስ በዕለተ ዓርብ በሚነበበው ግብረ ሕማም ላይ እንደተጻፈው ቅዱስ ዑራኤል ያንን ክቡር ደም በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በዓለም ሁሉ ላይ የረጨ መልአክ ነው። በእነዚህ ታላላቅ አገልግሎቶቹ ምክንያት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የመልአኩን መታሰቢያ በዓላት በተለያዩ ወቅቶች ታከብራለች፦
- ሐምሌ ፳፪ ቀን፦ ለዕዝራ ሱቱዔል ዕውቀትንና ጥበብን ያደለበትን እና ተአምራት ያደረገበትን ዕለት በማሰብ የሚከበር ዓመታዊ ንግሥ።
- ጥር ፳፪ ቀን፦ ሊቀ መላእክት ሆኖ የተሾመበትን ታላቅ ክብር በማሰብ የሚከበር በዓል ነው ።
- መጋቢት ፳፯ ቀን፦ በዕለተ ዓርብ ከጌታችን ጎን የፈሰሰውን ክቡር ደም በጽዋዕ የተቀበለበትን ታላቅ ምሥጢር በማሰብ የሚከበር በዓል ነው።
በአጠቃላይ፣ ሊቀ መልአክ ቅዱስ ዑራኤል በሥነ-ፍጥረት ሥርዓት፣ በጥበብና እውቀት መገለጥ፣ እንዲሁም በሰው ልጅ መጽናናትና ድኅነት ውስጥ ታላቅ ሚና ያለው የእግዚአብሔር ታማኝ አገልጋይ ነው። አማላጅነቱና ተራዳኢነቱ አይለየን፤ አሜን!
«በጊዜውም ባለጊዜውም ጽና» (፪ኛ ጢሞ. ፬፥፪)
ከዲያቆን አብርሃም ባንቲሁን
የተወደዳችሁ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምና ፍቅር ከሁላችን ጋር ይሁን። በየዓመቱ ሐምሌ፲፱ ቀን በታላቅ መንፈሳዊ አከባበር የምናከብረው የሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ፣ የእናቱ የቅድስት ኢየሉጣና የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል አምላካችን እግዚአብሔር በሰላም አድርሶናልና፤ እንኳን አደረሳችሁ!
ይህ በዓል ከአካዳሚክ ትምህርታችሁ ለዕረፍት ወጥታችሁ ወደ ቤተሰቦቻችሁ አሊያም ለተለያዩ ተግባራት በተሰማራችሁበት በዚህ በክረምት ወቅት የሚከበር በመሆኑ፣ በግቢ ውስጥ የነበራችሁን መንፈሳዊ ሕይወት፣ ጸሎትና አንድነት ከግቢ ውጭ ባለው ዓለም ውስጥ በተግባር የምታሳዩበትና የእምነታችሁን ጽናት የምትመሰክሩበት አጋጣሚ ነው።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ «ቃሉን ስበክ፤ በጊዜውም ባለጊዜውም ጽና» (፪ኛጢሞ. ፬፥፪) ብሎ ሲመክረው ብዙ ፈተና እንደሚገጥመው አውቆ ለሚመጣበት ፈተና እንዲዘጋጅ ነው።
“በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ” (ዕብ. ፲፩፥፴፯) ሐዋርያው ይህንን ያለው በሃይማኖታቸው መከራ የተቀበሉ ሰማዕታተ ብሉይ ከአቤል ጀምሮ ያሉትን ከዘረዘረ በኋላ ነው።
“አክሊለ ሰማዕታት፣ የሰማታት አክለል” አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ሲመላለስ ዘመኑ ሁሉ በመከራ ነው ያሳለፈው፤ በእርሱ እንደደረሰ በተከታዮቹ ሁሉ እንደሚደርስ ደግሞ ሲነግረን “በእርጥብ እንጨት እንዲህ የሚያደርጉ ከሆኑ፥ በደረቀውስ እንዴት ይሆን?” (ሉቃስ ፳፫፥፴፩) አለ። በዚህም መሠረት ሐዋርያት ሁሉ በመከራ አለፉ፤ ቅዱስ ጳውሎስ “እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ።” (፩ኛ ቆሮ. ፲፩፥፩) እንዲል አምላክን መስሎ እኛም እርሱን እንድንመስል መከረን።
“ምስክሮችህ ድንቆች ናቸው፤ ስለዚህ ነፍሴ ፈለገቻቸው።” (መዝ. ፻፲፱፥፻፳፱) እንዲል ልበ አምላክ ዳዊት ጨክነው ሰውነታቸውን ለመከራ የሰጡ ብዙዎች ናቸው። እስከጌታችን ዳግም ምጽአት ድረስ ስትሰበክ የምትቆየው ወንጌለ መንግሥት የምትሰበከው በብዙ መከራ ነውና “የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፥ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው።” (ዕብ. ፲፫፥፯) እያለ ሐዋርያው በአገልግሎት እየጸናን በግብር መከተል እንዳለብን ይመክረናል።
በዚህ መሠረት የክርስቶስ ፈለግ የተከተሉ ወንጌልን በሕይወታቸው የተረጐሙት ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ተጠቃሾች ናቸው።
ሐምሌ ፲፱ ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ የተቀበሉበት ቀን ነው፡፡ ሕፃኑ ዕድሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው እናቱ ከሮሜ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር ይዛው ሸሸች፤ በዚያም የሸሸችውን መኮንን እለ አስክንድሮስን አገኘችው፡፡ ሰዎችም ነገር ሠሩባት፤ ወደ እርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት፡፡
ቅድስት ኢየሉጣም «መኮንን ሆይ! ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ፤ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ» አለችው፡፡
ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስም ወደ እርሱ በመጣ ጊዜ ንጉሡ ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየና «አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ! እንዴት ነህ? » አለው፡፡ ሕፃኑም መልሶ «አዎ፣ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል፤ ለአንተ ግን ኀዘን፣ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ነው» አለው፡፡ እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና በዚያ ያሉትን እስከሚያስደነግጣቸው ድረስ ንጉሡን፣ መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው፡፡
መኮንኑም በአፈረ ጊዜ በውስጡ ሰም፣ ጨው፣ ሙጫ፣ የዶሮ ማር፣ እርሳስ፣ ብረት፣ ቅንጭብና ቁልቋል ጨምረው ታላቅ የብረት ጋን እንዲያፈሉ አዘዘ። ፍላቱም በ፲፬ ክንድ ያህል ከፍታ ወደ ላይ ይዘል ነበር።
ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ በእስር ላይ ሳሉ ወደዚህ የፈላ ጋን ውስጥ እንዲጣሉ ተወሰዱ። ቅድስት ኢየሉጣ የፍላቱን ጩኸት በሰማች ጊዜ ብትሸበርም፣ ልጇ ቅዱስ ቂርቆስ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ተሞልቶ አጸናት፤ ወደ እግዚአብሔርም ስለ እናቱ ጽናት አሳስቦ ጸለየ። ጸሎቱም ተሰምቶ እናቱ ጥንካሬን አገኘች።
ወደ ፈላው ጋን ውስጥ በተጣሉ ጊዜም ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ የብረቱን ጋን እሳት አጠፋው፤ ቅዱሳኑንም ሳይቃጠሉ አዳናቸው።
መኮንኑም አሳቡ ስላልተሳካ ፲፬ የሾሉና የጋሉ ብረት ችንካሮች አምጥተው ሰባቱን በእናቱ አካል፣ ሰባቱን ደግሞ በሕፃኑ አካል ላይ እንዲቸነክሩ፣ የሕፃኑንም የራስ ቆዳ ገፈው እሳት ውስጥ እንዲጨምሩ አዘዘ። አሁንም መልአኩ መጥቶ መከራውን አራቀለት። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ወርዶ አጽናናው፤ ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ታላቅ ቃል ኪዳን ሰጠው።
የተከበራችሁ የግቢ ጉባኤ ልጆች ከበዓሉ ልንወስዳቸው የሚገቡ ብዙ መንፈሳዊ ትምህርቶች አሉ፤ ጥቂቱን ለማንሣት ያህል የቅዱስ ቂርቆስ መንፈሳዊ ድፍረት፣ በነገሥታት ፊት ሳይፈራ በእምነት መቆም እንዲሁም ዓለማዊ ጫናዎችን በጸሎትና በእውቀት መመከት ነው።
የቅድስት ኢየሉጣ ጽናት፡ የሥጋ ፍርሃትን ማሸነፍ፣ መንፈሳዊ ሕይወትን ከዓለማዊ ጥቅም ማስቀደም እና ትውልድን በሃይማኖት ኮትኩቶ ማሳደግን እንዲሁም የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት፣ እግዚአብሔር ለሚታመኑበት ሁሉ ቅርብ አምላክ መሆኑንና መላእክቱን ልኮ እንደሚያድናቸው ማመን እንዳለብን የሚያስተምር ሕይወት ነው።
ታዲያ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በዚህ በክረምት ወቅት በዩኒቨርሲቲ ቆይታችሁ የነበራችሁን መንፈሳዊ ንቁ ተሳትፎ በክረምት ወቅትም አጠናክራችሁ መቀጠል አለባችሁ፤ በጊዜውም ባለጊዜውም መጽናት ከእነዚህ ሰማዕታት ተምራችኋልና፤ የተወደዳችሁ ተማሪዎች!
በዚህ በክረምት ወቅት ከዓለማዊ ፈተናዎችና ከከንቱ የሥጋ ፍላጎቶች ተጠብቃችሁ መንፈሳዊ ማንነታችሁን የምታጠናክሩበት፣ ለእግዚአብሔርና ለቤተክርስቲያን ሕይወት ቅድሚያ የምትሰጡበት ጊዜ መሆን አለበት።
የሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ መንፈሳዊ ድፍረት፣ የቅድስት ኢየሉጣ ጽናትና የሊቀ መላእክት የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት በየዕለት እርምጃችሁ አይለያችሁ። «የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር በቅዱስ ቂርቆስና በቅድስት ኢየሉጣ ጸሎት ይማረን፤ የተራዳኢው መልአክ የቅዱስ ገብርኤል ጥበቃና በረከት አይለየን! ለቅዱሳኑ የሰጠው አምላካዊ ቃል ኪዳንና በረከታቸው ከሁላችን ጋር ለዘላለሙ ይሁኑ።»
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር፤ አሜን
ሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) ጥቅሙና ጉዳቱ
ከመምህር ሓጋዚ አብርሃ
ባለንበት ዘመን ማኅበራዊ ሚዲያ በወጣቱ መንፈሳዊ ሕይወት፣ ሥነ ምግባር፣ ሥርዓተ ትምህርት እና ሥነ-ልቡናዊ ሕይወት ላይ እያሳደረ ያለው ተጽዕኖ ከፍተኛ ነው። ማኅበራዊ ሚዲያ በራሱ መሣሪያ ነው፤ መሣሪያ ደግሞ እንደ አጠቃቀማችን ወይ ይገነባናል ወይም ያፈርሰናል። “ከአያያዝ ይቀደዳል ከአነጋገር ይፈረዳል” እንዲሉ አበው አእምሮ ያለን አገናዛቢ፣ ልብም ያለን አሳቢ ፍጡር ነን። ከዚህ የተነሣ ይጠቅሙናል፣ ድካማችንን ይቀንሱልናል ብለን ያዘጋጀናቸው መሣሪያዎች እንዳሰብነው ሳይሆን አሉታዊ ተጽዕኗቸው ሲጨምር ከአጠቃቀማችን አንጻር ቆም ብሎ ማሰብ ያለብን እኛው የሰዎች ልጆች ነን። “ሰው ሠራሽ አስተውሎት” (AI) በተመለከተ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች አኳያ በትንታኔ ለማየት እንሞክራለን።
- ሰው ሠራሽ አስተውሎት ምንድ ነው?
ሰው ሠራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) በሰዎች የሚሠሩ፣ ማሰብና ማገናዘብ የሚችሉ ተደርገው የተዘጋጁ የኮምፒውተር ሥርዓቶች ወይም ፕሮግራሞች ማለት ነው።
በሌላ አገላለጽ፦ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሰጠውን የማሰብና የመማር ችግሮችን መፍታትና ውሳኔ መስጠት የሚያስችለውን አእምሯዊ ብቃት (Intelligence) የሰው ልጅ ደግሞ ማሽኖች (ኮምፒውተሮች) እንዲመስሉት አድርጎ የፈጠረው ጥበብ ነው።
ለምሳሌ፡- ChatGPT፣ የትርጉም ሥርዓቶች፣ የምክር አልጎሪዝሞች (recommendation algorithms) ፣ አውቶማቲክ የምርምር መሣሪያዎች፣የድምፅ ረዳቶች፣ ምስል አመንጪዎች (image generators) ፣ እና የትምህርት ሶፍትዌሮች ተጠቃሾች ናቸው።
በቅርብ ዓመታት ውስጥ “ሰው ሠራሽ አስተውሎት” (AI) በትምህርት፣ በኮሙኒኬሽን፣ በምርምር እና በዕለት ዕለት የሰው ልጆች ሕይወት ውስጥ ካሉ ተፅዕኖ ፈጣሪ መሣሪያዎች አንዱ ሆኗል። ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶችን ጨምሮ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንደ ቻትቦቶች (chatbots)፣ የምርምር ረዳቶች፣ የትርጉም መሣሪያዎች እና አውቶማቲክ የመማሪያ መድረኮችን የመሳሰሉ የ-AI ሥርዓቶችን በስፋት እየተጠቀሙ ይገኛሉ። ምንም እንኳን AI ብዙ ጥቅሞችን ቢሰጥም፣ ያለ አግባብ ከተጠቀምንበት ወይም ከልክ በላይ በእሱ ላይ ከተደገፍን ሥነ-ምግባራዊ እና መንፈሳዊ ጉዳቶችን ያስከትላል።
በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚማሩ የግቢ ጉባኤያት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች በሁለት አስፈላጊ ዘርፎች በተመሳሳይ ጊዜ የሕይወት ለውጥ እንዲያመጡና እንዲያድጉ ይጠበቃል።
- የትምህርት ጥራትና ብቃት ፡- በተሰማሩበት የትምህርት ዘርፍዕውቀትን፣ ጥበብን፣ ጥልቅ አስተሳሰብን እና ሙያዊ ብቃትን ማግኘትና ማሳደግ፤
- ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊ ሕይወት፡- በጾም፣ በጸሎት፣ በትምህርተ ሃይማኖት ዕውቀት፣ በትሕትና፣ በንስሓ እና በምሥጢራት ሱታፌ፣ በማስተዋልና በትዕግሥት፣ በቅድስና እና ከእግዚአብሔር ጋር ባለው ኅብረት መሳተፍና ማደግ ናቸው።
የፈጠራ ቴክኖሎጂ በራሱ ክፉ አይደለም። ችግሩ ያለው የሰው ልጅ የአጠቃቀም መንገድ ላይ ነው። ልክ እንደማንኛውም የሰው ልጅ ፈጠራ ሁሉ፣ AI ለበጎ ነገር የሚውል መሣሪያ ወይም የጉዳት ምንጭ ሊሆን ይችላል። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፦ “ሁሉ ተፈቅዶልኛል ፤ ሁሉ ግን አይጠቅምም”(፩ኛ ቆሮ. ፮፲፪) እንዳለው የግቢ ጉባኤያት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች AI-ን እንዴት በጥበብ፣ በተጠያቂነት እና ለመንፈሳዊ አገልግሎት መጠቀም እንደሚችሉ መረዳትና መገንዘብ ይገባል።
ቅዱስ መጽሐፍ “የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው።” እንዳለ (ምሳሌ ፱፥፲) በኦርቶዶክሳዊ የሥነ-መለኮት ትምህርት መሠረት እውነተኛ ጥበብ የሚገኘው ከእግዚአብሔር ነው። ሰው ሠራሽ አስተውሎት መረጃ ሊያቀናብር ይችላል እንጂ መሠረታዊ አካዳሚያዊ ጥበብን፣ ተግባራዊ ልምምድን ወይም የሰው ልጅ ኃላፊነትን ሊተካ አይችልም።
- የሰው ሠራሽ አስተውሎት ጥቅሞች
የግቢ ጉባኤያት ኦርቶዶክሳውዯን ተማሪዎች ሰው ሠራሸ አስተውሎትን በአግባቡ እና በኃላፊነት ስሜት ጥቅም ላይ ማዋል ከቻሉ በሚከተሉት ጉዳዮች በጣም ጠቃሚ ሊሆን ይችላል።
ሀ. ለትምህርት
- መረጃን በቀላሉ ማግኘት፡-
ሰው ሠራሽ አስተውሎትተማሪዎች መጻሕፍት፣ የምርምር ጽሑፎች፣ ማብራሪያዎች፣ የቋንቋ ትርጉሞች እና ማጠቃለያዎች በፍጥነት እንዲያገኙ ይረዳል። ይህ የመማር ብቃትንና ፍጥነትን ሊያሻሽል ይችላል።
- የምርምር እገዛ
ሰው ሠራሽ አስተውሎት ሐሳቦችን በማደራጀት፣ ረቂቅ ማውጫዎችን በማዘጋጀት፣ ዋቢ መጻሕፍትን በማስገኘት፣ ሰዋሰውን በማስተካከል፣ ረጅም ጽሑፎችን በማጠቃለል፣ እና መረጃዎችን በመተንተን ተማሪዎችን ሊረዳ ይችላል። እንዲሁም ለድኅረ-ምረቃ ተማሪዎች የሥነ-ጽሑፍ ክለሳ (literature review) ፣ የጽሑፍ ቅርጽ ማስተካከል ፣ የዋቢ ጽሑፎች አደረጃጀት (citation organization) ወ.ዘ.ተ ላይ ሊያግዝ ይችላል።
- የቋንቋ እና የተግባቦት ድጋፍ
በባዕድ ቋንቋዎች የሚቸገሩ ተማሪዎች ሰው ሠራሽ አገልግሎት ለትርጉም፣ ለሰዋስው እርማት፣ ቃላትን ለመማር እና ለአካዳሚክ ጽሑፍ ድጋፍ መጠቀም ይችላሉ።
- የጊዜ ቁጠባ
በተለምዶ ብዙ ሰዓታት የሚወስዱ ሥራዎች አንዳንድ ጊዜ በ-AI እገዛ በፍጥነት ሊጠናቀቁ ይችላሉ፤ ይህም ተማሪዎች ይበልጥ ጥልቅ በሆነ ጥናትና ትንተና ላይ እንዲያተኩሩ ዕድል ይሰጣል።
ለ. ከቤተክርስቲያን እና መንፈሳዊ ሕይወት ጋር የተያያዙ ጥቅሞች
ሰው ሠራሽ አስተውሎት በጥንቃቄ ጥቅም ላይ ሲውል ለቤተክርስቲያን አገልግሎት እና ለመንፈሳዊ ትምህርት ሊያግዝ ይችላል።
- መንፈሳዊ ትምህርቶችን ለማግኘት
የክፍተኛ ትምህርት ተቋማት የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሰው ሠራሽ አስተውሎትን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችን ለመፈለግ፣ የቀደሙት ሊቃውንትና የቅዱሳን አባቶችን ጽሑፎች ለማግኘት፣ የቤተክርስቲያንን ታሪክ ለመማር፣ ኦርቶዶክሳዊ ሥነ-መለኮትን ለማጥናት ሊጠቀሙበት ይችላሉ።
- ለሐዋርያዊ አገልግሎት (ለትምህርታዊ አገልግሎት)
የቤተክርስቲያን መምህራንና አገልጋዮች ሰው ሠራሽ አገልግሎትን ትምህርቶችን ለማዘጋጀት፣ የማስተማሪያ ቁሳቁሶችን ለማደራጀት፣ ሰነዶችን ለመተርጎም፣ እና የኢንተርኔት (ኦንላይን) ስብከተ-ወንጌልን ለመደገፍ በሚገባ ሊገለገሉበት ይችላሉ።
- በቤተክርስቲያን ፈተናዎች እና ችግሮች ላይ ምርምር ለማድረግ
ከላይ ካየናቸው ጥቅሞች ከፍ ባለ መንገድ ከተመለከትነው ደግሞ ሰው ሠራሽ አስተውሎትን የግቢ ጉባኤያት አገልጋዮች በተለይ ድኅረ-ምረቃ ተማሪዎች ማኅበራዊ ፈተናዎችን ለመተንተን፣ የወጣቶችን ችግሮች ለመመርመር፣ የግቢ ጉባኤያት እና የሰንበት ትምህርት ቤቶችን የአገልግሎት አካሄድ ለማጥናትና ለማዘመን፣ ከአኀት እና ሌሎች ምሥራቅ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ጋር የተያያዙ ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉ የአገልግሎት መፍትሔዎችን ለመቅረጽ ጥቅም ላይ ማዋል ይቻላል።
- የሰው ሠራሽ አስተውሎት ጉዳት
ምንም እንኳን ከላይ የተጠቀሱትንና ሌሎችም ጥቅሞች ቢኖሩትም፣ ሰው ሠራሽ አስተውሎት ያለ አግባብ ጥቅም ላይ ከዋለ በቀላሉ የማንወጣቸው ከባድ ጉዳቶችን ሊያስከትል ይችላል።
ሀ. ትምህርታዊ ጉዳቶች
- ጥገኝነት እና ምሁራዊ ስንፍና
ሰው ሠራሽ አስተውሎት አጠቃቀም ላይ ከሁሉ የላቀው አደጋ በእሱ ላይ ከመጠን በላይ መደገፍ ነው። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ በAI ላይ ሲደገፉ፦ በጥልቀት ማሰብ ያቆማሉ፤ ማንበብን ይተዋሉ፤ የማሰብ (የመተንተን) ችሎታቸውን ያጣሉ፤ እናም የፈጠራ ብቃታቸው ይዳከማል። መማር ደግሞ ጥረትን፣ ሥርዓትን (ዲስፕሊንን) እና ልፋትን ይጠይቃል። ኦርቶዶክሳዊ የቅዱሳን አባቶች ሕይወት እንደሚያስተምረን አእምሮአዊም ሆነ መንፈሳዊ ዕድገት የሚመጣው በሥራና በትዕግሥት ነው።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ከእናንተ ጋር ሳለን፦ ሊሠራ የማይወድ ማንም አይብላ ብለን አዘናችሁ ነበርና።” (፪ኛ ተሰ. ፫፥፲) እንዳለ ሰው ሠራሽ አስተውሎት ማሰብን ሊያግዝ ይገባል እንጂ ሊተካው አይገባም።
- የምርምር ክሂሎት መዳከም
እውነተኛ ምርምር ጥያቄ መጠየቅን፣ ማጣራትን፣ ማነጻጸርን፣ መተንተንን፣ እና የራስን አዲስ ትንታኔ ማቅረብን ይጠይቃል። ተማሪዎች በ-AI የተፈጠረውን ጽሑፍ ዝም ብለው የሚገለብጡ ከሆነ ፡- የምርምር ዘዴን ማዳበር ያቅታቸዋል፤ የአካዳሚክ ታማኝነትን ያጣሉ። ከዚህ የተነሣ ራሳቸውን ችለው ሳይንሳዊ ሥራዎችን መሥራት የማይችሉ ይሆናሉ። በመጨረሻም እንዲህ ዓይነቶቹ ተማሪዎች ዲግሪ ሊይዙ ይችላሉ፤ ነገር ግን እውነተኛ ብቃት አይኖራቸውም።
- የሌሎችን ሥራ መስረቅ (Plagiarism) እና አካዳሚካዊ ታማኝነት ማጣት
በሰው ሠራሽ አስተውሎት-AI የተዘጋጀን ሥራ ያለ ምንም ግምገማ ወይም ምንጩን ሳይጠቅሱ በቀጥታ መቅዳት የስርቆት እና የሐሰተኝነት መገለጫ ነው። አካዳሚካዊ ታማኝነት እውነተኛነትንና ኃላፊነትን ይጠይቃል። የኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊነትም ሐሰትን በጥብቅ ይከለክላል። በቅዱስ መጽሐፍ “ስለዚህ ውሸትን አስወግዳችሁ፥ … እያንዳንዳችሁ ከባልንጀሮቻችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ።” (ኤፌ. ፬፥፳፭) እንዳለ አንድ ክርስቲያን ተማሪ ለምቾት ሲል እውነትን አሳልፎ መስጠት የለበትም።
- የተሳሳተ መረጃ እና ዕውቀት
ሰው ሠራሽ አስተውሎት አንዳንድ ጊዜ ትክክል ያልሆኑ መረጃዎችን፣ ተሳሳቱ ዋቢ መጻሕፍትን፣የተዛቡ ትርጓሜዎችን ወይም ወገንተኝነት ያለባቸውን ድምዳሜዎች ያመነጫል። እንዲሁም መንፈሳዊ ምሥጢራትን ወይም ታሪካዊ እውነታዎችን በትክክል ላይረዳ ይችላል። የነገረ መለኮት (Theology) ዕውቀትን ከሰብአዊ ፍልስፍና ጋር በመደባለቅ የተሳሳተ ድምዳሜ ሊሰጥ ይችላል።
ለ. ከቤተክርስቲያናዊ ሕይወት አኳያ የሚያስከትላቸው ጉዳቶች
ቶሎ ማስተዋልና መረዳት ካልተቻለ በAI ምክንያት በሚያጋጥሙ ፈተናዎችበመንፈሳዊ ሕይወት የሚደርሰው ጉዳት ከአካዳሚክ ጉዳት የከፋ ሊሆን ይችላል። ለዚዚህም የሚከተሉትን ማሳያዎች እንመልከት፡-
- የግል መንፈሳዊነት መዳከም
ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊነት ክርስቲያናዊ ተጋድሎን፣ ሥርዓትን ፣ ትዕግሥትን፣ ትኩረትን፣ ጽናትንና ትጋትን እጅጉን ይፈልጋል። ለፈጣን የቴክኖሎጂ እገዛ ሁል ጊዜ መገዛት ትዕግሥትን፣ ጸጥታን፣ የተመስጦ ሕይወትን፣ ጥልቅ ሱባኤን ወዘተ. ሊያዳክም ይችላል።
- ከቤተክርስቲያን ኅብረት እና ከአባቶች ምክር መለየት
ከልክ ያለፈ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ጥገኛ መሆን ከቅድስት ቤተከርስቲያን ኅብረታዊና ሥርዓተ-አምልኮ ሕይወት፣ ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ምክርና ኑዛዜ ከቤተክርስቲያን ትውፊት ወዘተ. ቀስ በቀስ ሊነጥለን እና ሊያርቀን ይችላል።
- ትዕቢት እና የዕውቀት ቅዠት
መረጃን በቀላሉ ማግኘት ምሁራዊ መታበይን ሊፈጥር ይችላል። ‘መረጃዎችን ወዲያውኑ ማግኘት ስለምችንል ሁሉንም ነገር አውቃለሁ’ ወደሚል ግልብ ሕይወት ሊመራን ይችላል። ነገር ግን ያገኘነው መረጃ እንጂ ጥበብ አይደለም። የቤተክርስቲያን አባቶች ከትዕቢት እንድንጠበቅ ደጋግመው ያስጠነቅቃሉ። ትዕቢት መንፈሳዊ ማስተዋልንና ጥበበ እግዚአብሔርን ሊያጨልም ይችላልና።
- ጸጥታ እና የውስጥ ትኩረት ማጣት
የዘመኑ ቴክኖሎጂዎች አእምሮን ዘወትር ያነቃቁታል። ከመጠን በላይ በዲጂታል ነገሮች ላይ ጥገኛ መሆን የውስጥ ጸጥታን (እርጋታን)፣ ማሰላሰልን፣ ጸሎትን እና ለእግዚአብሔር የሚሰጠውን ትኩረት ያዳክማል።
- የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች AIን እንዴት እንጠቀም?
መጽሐፍ ቅዱስ “ሁሉን ፈትኑ መልካሙንም ያዙ” ይላል። (፩ኛ ተሰ. ፭፥፳፩) የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ቴክኖሎጂውን እንደ ጌታ ሳይሆን እንደ አገልጋይ ሊጠቀሙበት ይገባል።
- AIን እንደ ማሟያ መሣሪያ ብቻ መጠቀም
ተማሪዎች ለሚፈልጓቸው ጉዳዮች መጻሕፍትን በራሳቸው ማንበብ፣ የራሳቸውን ትንታኔ መጻፍ፣ በሂሳዊ መንገድ መመልከት እና AI-ን የመማር ሂደታቸውን ለመደገፍ ብቻ መጠቀም አለባቸው። በመሠረታዊነት ጥሩ ትምህርት ጥያቄን፣ ጥረትን፣ መተንተን እና ሥርዓትን ይፈልጋል።
- መረጃዎችን በጥንቃቄ ማረጋገጥ
ተማሪዎች ከ-AI የሚያገኟቸው ምላሾችን ከአካዳሚክ መጻሕፍት፣ ከምርምር መጽሔቶች (journals)፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ፣ ከአባቶች ጽሑፎች፣ እና ከታመኑ ምሁራን ሥራዎች ጋር በማነጻጸርና በማመሳከር ጉዳዮችን በማስተዋል መጠቀም አስፈላጊ ነው።
- የቤተክርስቲያን ሥርዓትን መጠበቅ
የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ምን ጊዜም ቴክኖሎጂን ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮና ሥርዓት ሥር አድርገውና አስማምተው መጠቀም ላይ ቆራጥ መሆን ይጠበቅባቸዋል። በተለይ የጾም፣ የጸሎት፣ የንስሐና የምሥጢራት ሕይወትን፣ የቅዳሴና የሥርዓተ አምልኮ ሱታፌን፣ የቅዱሳት መጻሕፍት ንባብ ሕይወትን ወዘተ. የAI አገልግሎት ጊዜ እንዲተካባቸው በፍጹም መፍቀድ የለባቸውም።
- እውነተኛ ጥናትና ምርምር ማድረግ
የግቢ ጉባኤያት አመራር እና ተመራቂ ተማሪዎች በተለይ የድኅረ-ምረቃ ተማሪዎች የመመረቂያ ጽሑፍ (thesis) በሚጽፉበት ጊዜ በቀጥታ ከ-AI የመቅዳት ፈተና ይገጥማቸዋል። ይህ ትልቅ አካዳሚያዊና መንፈሳዊ ችግሮችን ይፈጥራል። ይልቁንም ተማሪዎች AI-ን በኃላፊነት ስሜት ሊጠቀሙበት ይገባል።
AI ለምናደርጋቸው ጥናቶችና ምርምሮች የጽሑፍ ቅርጽ (formatting)፣ ማውጫዎች፣ ማጠቃለያዎች፣ እና አደረጃጀትን በመስጠትና በመፍጠር ሊያግዝ ይችላል። ነገር ግን ክርክሮች (arguments)፣ ትንታኔዎች (analysis)፣ ትርጓሜዎች (interpretation)፣ እና ድምዳሜዎች (conclusions) ወ.ዘ.ተ ከተማሪ ከራሱ ምሁራዊ ጥረት መምጣት አለባቸው።
ይልቁንም ጠንካራ ምርምር እውነተኛ ችግሮችን እንደሚፈታ በማመን ሰዎችን ቃለ-መጠይቅ ማድረግ፣ የመስክ መረጃዎችን መሰብሰብ፣ የቤተክርስቲያንን ነባራዊ ሁኔታዎች መታዘብ፣ የአካባቢውን ችግሮች መተንተን፣ እና ከእውነተኛ የሚመለከታቸው አካላት/ማኅበረሰብ ጋር በመገናኘት የተፈተነና የታሸ የጥናትና ምርምር ውጤት ባለቤት መሆን መቼም ሊዘነጋ አይገባውም።
በቤተ ክርስቲንና ኦርቶዶክሳውን ሕይወት ታሳቢ ሊሆኑ የሚችሉ የጥናትና ምርምር መስኮች፦
- የወጣቶች መንፈሳዊ ተጋድሎ (ፈተናዎች)፣
- የቴክኖሎጂ ሱስ፣
- የቤተክርስቲያን ጥንታውያን መጻሕፍትንና የብራና ጽሑፎችን በዲጂታል መንገድ የመጠበቂያ (Archiving) ሥርዓት
- የግእዝ ቋንቋን ጠብቆ ማቆየት፣
- የዲጂታል ስብከተ-ወንጌል አገልግሎት
- ሥነ-ምግባራዊ የ-AI አጠቃቀም፣
- የአእምሮ ጤና እና መንፈሳዊነት፣
- ጥናትና ምርምር ለቤተክርስቲያን ያለው ፋይዳ
- የቤተክርስቲያን አስተዳደር ሥርዓቶች የተወሰኑት ናቸው።
- አካዳሚክ ጥራትን ከመንፈሳዊ ሕይወት ጋር ማዋሐድ
ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳሪያ “ለመንፈሳዊ ሕይወት የሚጠቅመንን ዕውቀት ከዓለማውያን መጻሕፍትም ቢሆን መቅሰም አለብን” እንዳለው፣ ትምህርት የሰውን ልጅ ወደ በጎነት እና ወደ እውነት ሊመራው ይገባል። ስለዚህ በግቢ ጉባኤያት የሚያልፉ ምሁራን እውነትን፣ ትሕትናን፣ ታማኝነትን፣ አገልጋይነትን … ገንዘብ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ከእነዚህ መንፈሳዊ ዕሴቶች ውጭ የሆነ ዕውቀት የትም ሊያደርስ አይችልም። ያለ እግዚአብሔር የሚደረግ የሰው ልጅ እድገት አደገኛ እንደሆነ ቤተክርስቲያን ታስተምራለች። ቴክኖሎጂ የሰውን ልጅ ከኃጢአት፣ ከሞት፣ ከራስ ወዳድነት፣ ከትዕቢት ወይም ከመንፈሳዊ ባዶነት ሊያድነው አይችልም። የሰውን ልብ በበጎነት የሚለውጠው እና ወደ ፍጹም ድኅነት የሚያደርሰው እግዚአብሔር ብቻ ነው።
ቅዱስ መጽሐፍ “ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጠፋ ምን ይጠቅመዋል?” (ማር. ፰፥፴፮) እንዳለ ሰው ሠራሽ አስተውሎት (AIን) ስንጠቀም መንፈሳዊ ማንነታችንን በማያጠፋ እና ለአካዳሚክ ስኬታችን ድጋፍ በሚሰጥ ሚዛን ላይ መሆን አለበት።
በአጠቃላይ ሰው ሠራሸ አስተውሎት (AI) ለክርስቲያኖች በጎ ዕድልም ፈተናም ነው። ሙሉ በሙሉ በጎ ወይም ሙሉ በሙሉ ክፉ አይደለም። ጥቅሙ የሰው ልጅ በሚጠቀምበት መንገድ ላይ የሚወሰን ነው። የግቢ ጉባኤያት ወጣት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ቴክኖሎጂውን በጥንቃቄና በኃላፊነት ስሜት በመጠቀም፣ በአንድ እጃቸው የሳይንስ ዕውቀታቸውን፣ የምርምር ጽሑፎቻቸውን፣ በሌላ እጃቸው ደግሞ የቤተከርስቲያን አገልግሎትና መንፈሳዊ ሕይወትን ይዘው፣ ለቤተክርስቲያንና ለሀገር የሚተርፍ ብሩህ አእምሮና ንጹሕ ልብ ያላቸው ምሁራን ሆነው መውጣት የምችሉባቸው ሁኔታዎች እንዳሉ በመረዳት ጊዜው እና ቴክኖሎጂውን በአግባቡ መጠቀም ይጠበቅባቸዋል።
“በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው” (ሐዋ. ፪ ፥፬)
ከመምህር ተፈሪ መንገሻ
የተወደዳችሁ የክርስቶስ ቤተሰቦች እንደምን ሰነበታችሁ? አሜን፣ የአባቶቻችን አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን። እንኳን ለበዓለ ሃምሳ (በዓለ ጰራቅሊጦስ) አደረሳችሁ።
ቅዱስ ሉቃስ በሐዋርያት ሥራ ላይ እንደጻፈልን፣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ለዓርባ ቀናት ለደቀ መዛሙርቱ እየተገለጠ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ነገራቸው። በዓርባኛው ቀን ሲያርግ እንዲህ አላቸው፦ “ወናሁ አነ እፌኑ ተስፋሁ ለአቡየ ላዕሌክሙ ወአንትሙሰ ንበሩ ሀገረ ኢየሩሳሌም እስከ ትለብሱ ኃይለ እምአርያም፤እነሆም፥ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ።” (ሉቃስ ፳፬፥፵፱)
እነርሱም የታዘዙትን ጠብቀው፣ በሃምሳኛው ቀን (በዓለ ጰንጠቆስጤ) በማርቆስ እናት በቅድስት ማርያም ቤት በአንድ ልብ ሆነው በጸሎት ሳሉ፣ ድንገት እንደ ዓውሎ ነፋስ ያለ ድምፅ መጣ፤ የእሳት ላንቃዎችም በእያንዳንዳቸው ላይ ዐረፉ። መጽሐፉ እንደሚለን፦ “በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው።”
ሀ. በመንፈስ ዘንድ መድልዎ የለም
በዚያች ዕለት መለኮታዊው እሳት የወረደው በጥቂቶቹ ላይ ብቻ አይደለም፤ “በሁሉም” ላይ ነው እንጂ። ይህም መለኮታዊ ጸጋ በዘር፣ በባህል፣ በጾታ ወይም በማኅበራዊ ደረጃ ሳይገደብ ለሰው ልጆች ሁሉ በነጻ የተሰጠ መሆኑን ያሳያል። ነቢዩ ኢዩኤል በትንቢቱ ላይ፦ “ከዚህም በኋላ እንዲህ ይሆናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈስሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ” (ኢዩ. ፪፥፳፰) እንዳለ፣ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ሁሉ ጸጋውን አበዛ።
በተለይ ከተለያየ አካባቢና ባህል የመጣችሁ ወጣቶችና ምእመናን፣ በመንፈስ ቅዱስ ጥላ ሥር ሁላችንም እኩል መሆናችንን ማወቅ አለብን።
በክርስቶስ ቤት ማግለል የለም፣ ሁላችንም በጥምቀት አንድ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ተቀበልን የአንድ አባት ልጆች ነን።
ለ) ጎዶሎዎቻችን
እኛስ? ጎዶሏችንን በምን እየሞላን ነው?
በዕለተ ጰራቅሊጦስ ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ ተሞልተው በደስታና በኃይል ሲመሰክሩ፣ በውጭ የነበሩት ሰዎች አላስተዋሏቸውም ነበር፤ ይልቁንም ፦ “ሌሎች ግን እያፌዙባቸው፦ ጉሽ የወይን ጠጅ ጠግበዋል አሉ።” (ሐዋ. 2፥13) ተብሎ ተጽፏል። ቅዱስ ጳውሎስም ይህንን ምሥጢር ሲተረጉም ፦ “በመንፈስ ተሞሉ እንጂ በወይን ጠጅ አትስከሩ ይህ ማባከን ነውና” ይላል።(ኤፌሶን ፭፥፲፰)
ይህ ጥልቅ ምሥጢር ነው። የሰው ልጅ በውስጡ ተፈጥሮአዊ የሆነ የመለኮታዊ ደስታ ጥማት አለው። ይህንን ጥማት ግን በምድራዊ ሱሶች (በአልኮል፣ በዕፅ፣ በቁማር፣ በማኅበራዊ ሚዲያ ሱስ፣ በዝሙት ወዘተ) ለመሙላት ሲሞክር ሕይወቱን ያባክናል። የመንፈስ ቅዱስ ሙላት ግን የሰውን ውስጣዊ ጥማት መለኮታዊ በሆነ ሰማያዊ ደስታ ስለሚሞላው፣ ሰውየው ምድራዊውን ሱስና የኃጢአት ሕይወት ሙሉ በሙሉ እንዲጠላና ነጻ እንዲወጣ ያደርገዋል። ዓለም በሐሰተኛ ወይን ታሰክራለች፤ ጰራቅሊጦስ ግን በእውነተኛ የሕይወት ደስታ ይሞላል!
ሐ. አንድነትና ስምምነት
ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ከመውረዱ በፊት “በአንድ ልብ ሆነው በአንድነት” ተሰብስበው ነበር። ይህ የሚያሳየው መንፈስ ቅዱስ የሚሠራውና የሚሞላው መለያየትና ክፋት ባለበት ቦታ ሳይሆን፣ ሰዎች በፍቅር፣ በይቅርታና በአንድነት ሲቆሙ መሆኑን ነው። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ፦ “በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ” (ኤፌ. ፬፥፫) በማለት ያሳስበናል። በማኅበራችን፣ በቤታችንና በጉባኤያችን ውስጥ ክፋትንና መለያየትን አውጥተን ስንጥል፣ ያን ጊዜ መለኮታዊው እሳት በውስጣችን ያድራል።
መ. አዲስ ልሳንና የቋንቋ መታደስ
በብሉይ ኪዳን የሰው ልጅ እግዚአብሔርን ለመፎካከር የባቢሎንን ግንብ በገነባ ጊዜ፣ እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ደባልቆ በተበተኑ ጊዜ ቋንቋ የቅጣት ምልክት ነበረ።(ዘፍ.፲፩÷፩-፰) ነገር ግን በዕለተ ጰራቅሊጦስ መንፈስ ቅዱስ ሲወርድ ቋንቋዎችን አላጠፋቸውም፤ ይልቁንም ሐዋርያት ከተለያየ ዓለም በመጡ ሕዝቦች ቋንቋ እንዲናገሩ አደረገ። “…እኛ እያንዳንዳችን የተወለድንበትን የገዛ ቋንቋችንን እንዴት እንሰማለን?” ይላል።(ሐዋ. ፪፥፰)
ይህ ምሥጢር ምን ያሳየናል? መንፈስ ቅዱስ የሰውን ልጅ ማንነትና ባህል አያጠፋም፣ ይቀድሰዋል እንጂ። ዛሬ በሀገራችን በብሔርና በባህል ልዩነት ምክንያት ሰይጣን ትውልዱን በሚያባላበት ዘመን፣ ጰራቅሊጦስ መንፈስ ቅዱስ ልዩነቶቻችንን ሳያጠፋ በፍቅር ልዩነትን ውበት የሚያደርግ የመለኮታዊ አንድነት ኃይል ነው። የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት ሰው የሌላውን ልዩነት እንደ መለኮታዊ ስጦታ እንጂ እንደ ጠላትነት አይመለከትም።
ሠ. የፍርሃት መወገድ
ከመንፈስ ቅዱስ መውረድ በፊት ደቀ መዛሙርቱ በአይሁድ ፍርሃት ዝግ በሆነ ቤት ውስጥ ተሸሽገው ነበር። ሐዋርያት ጌታቸውን አይተውታል፣ ትንሣኤውን አውቀዋል፤ ነገር ግን በውስጣቸው መንፈሳዊው ኃይል ስላልነበረ በፍርሃት ቆፈን ተይዘው በቤት ውስጥ ተሸሽገው ነበር። ዛሬም ብዙ ክርስቲያኖችና ወጣቶች ስለ ነገ ሕይወታቸው፣ ስለ ሥራ ማጣት፣ ስለ በሽታና ስለ ሞት በፍርሃት ዝግ በሮች ጀርባ ተቀምጠዋል።
መንፈስ ቅዱስ ሲሞላባቸው ግን ፍርሃታቸው ተወግዶ በሕዝብ ፊት ወጥተው በድፍረት መመስከር ጀመሩ። ቅዱስ ጳውሎስ ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ ሲጽፍለት፦ “እግዚአብሔር የኃይልና የፍቅር፣ ራስንም የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንምና” ይላል። (፪ኛ ጢሞ. ፩፥፯)።
የእሳት ላንቃዎች በእያንዳንዳቸው ላይ ባረፉ ጊዜ፣ ያ አይሁድን ይፈራ የነበረው፣ ጌታውን የካደው ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ዝግ የነበሩትን በሮች ከፍቶ ወጣ!
በሺዎች የሚቆጠሩ አይሁድ በነበሩበት አደባባይ ላይ ቆሞ፣ ድምፁን ከፍ አድርጎ በድፍረት መመስከር ጀመረ። (ሐዋ. ፪፥፲፬) ይህ የሚያሳየው ፍርሃት የሚወገደው በመለኮታዊው እሳት መሆኑን ነው። መንፈስ ቅዱስ ወደ ልብ ሲገባ ፍርሃት ቦታ የለውምና ተበትኖ ይጠፋል።
ወጣቶች ሆይ በመንፈስ ቅዱስ ራሳችንን እንግዛ!
ፍርሃት አእምሮን ያውካል፤ የተሳሳተ ውሳኔ እንድንወስንም ያደርገናል። ይህ መንፈስ ግን ለአእምሯችን መረጋጋትን፣ ማስተዋልንና ሰላምን ይሰጠናል። በማንኛውም ሁከት ውስጥ ሆነን ነገሮችን በእግዚአብሔር መነጽር እንድንመለከት ያደርገናል።
ስለዚህ ዛሬ በዚህ በበዓለ ጰራቅሊጦስ ልባችንን ለእግዚአብሔር መንፈስ እንክፈት። ጎዶሏችንን በዓለማዊና ጊዜያዊ ከንቱ ነገሮች ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ እንሙላ፤ ልዩነቶቻችንን በፍቅር አውርደን በአንድነት እንቁም፤ የፍርሃትንም ሰንሰለት ሰብረን በመንፈስ ቅዱስ በሚገኝ ኃይል፣ ፍቅርና ራስን በመግዛት እውነተኛ ነጻነትን እንኑር።ለዚህም አምላካችን እግዚአብሔር በቸርነቱ ያግዘን፡፡አሜን!
ስብሐት ለእግዚአብሔር!
ደብረ ምጥማቅ
ከመምህር አዲሱ በዛብህ
”አብ በሰማይ ሆኖ ተመለከተ፣ እንደ አንቺ ያለ አላገኘም፤ አንድ ልጁንም ልኮ ከአንቺ ሰው ሆነ።”
[ቅዳሴ ዘእግዚእትነ ማርያም]
ደብረ ምጥማቅ ከሠላሳ ሦስቱ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓላት አንዱ ነው። ደብረ ምጥማቅ በግብፅ ሀገር በምኔተ ገምኑዲ አቅራቢያ የምትገኝ ቦታ ናት። እመቤታችን በስደት ሳለች ጌታ በዚህ ቦታ በስምሽ ዐቢይ ቤተ ክርስቲያን ይታነጻል፤ ስሙንም ደብረ ምጥማቅ ይሉታል ብሎ ነግሯት ነበር። ይኸውም አልቀረ፤ በዚሁ ቦታ በእመቤታችን ስም ቤተክርስቲያን ታንጾ ስሙ ደብረ ምጥማቅ ተብሏል።
በዚህም ዕለት እመቤታችን ከፀሐይ ሰባት እጅ አብርታ ከጉልላቱ ላይ በመንበረ ብርሃን ተቀምጣ፣ መላእክት ሊቃነ መላእክት ከበው ሲያመሰግኗት፣ ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ጻድቃንና ሰማዕታት እጅ ሲነሷት ታይታለች። “እንዘ ትበርቂ በደብረ ምጥማቅ ሐምሰ ዕለታተ” እንዳለ ደራሲው በልጇ የመለኮት ብርሃን አሸብርቃ መላእክት: ሊቃነ መላእክት: ኪሩቤል: ሱራፌል ከበዋት ነቢያት: ሐዋርያት: ሰማዕታት: ደናግላን: መነኮሳት ሄሮድስ ያስፈጃቸው ሕፃናት ይመጣሉ፤ ሱራፌልም ማዕጠንት ይዘው በእያንዳንዱ እያመሰገኑ ያጥኑ ነበር። ከሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ በነጭ ፈረስ፣ ቀጥሎም ቅዱስ መርቆሬዎስ በጥቁር ፈረስ በየተራ እየመጡ ይሰግዱላታል።
ከፊቷ ብርሃን የተነሣ 5 ቀን ሌሊቱና ቀኑ አይታወቅም ነበር። በዚህ ጊዜ ልብሳቸውን ወደ ላይ ሲወረውሩላት የፈቀደችውን ተቀብላ ትልክላቸዋለች። ከዚያም ለበረከት ይካፈሉታል። ከተሰበሰቡትም እስኪ እገሌን አስነሺልን እያሉ ሲለምኗት አስነሥታ በሕይወተ ሥጋ ታሳያቸው ነበር። እንዲህ እየሆኑ በፍጹም ደስታ ሰንብተዋል። እስከ አምስት ቀንም ምእመናኑንም አረማውያኑንም አንድ ወገን አድርጋ ስትባርክ ሰንብታለች። ከዚህም በኋላ ምእመናኑም አረማውያኑም በየዓመቱ እነዚህን አምስት ዕለታት በደብረ ምጥማቅ ተሰብስበው የሚያከብሩ ሆነዋል። የበዓሉ መታሰቢያ ከግንቦት 21 እስከ 25 ቀን ነው።
ግንቦት 21 በደብረ ምጥማቅ በገሃድ ተገልጻ ታላቅ ተአምር ያደረገችበት፡፡
ግንቦት 22ና 23 በደብረ ምጥማቅ ለተሰበሰቡ ምእመናን በግልጽ በመታየት ትነጋገራቸው የነበበት፡፡
ግንቦት 24 እመቤታችን ተወዳጅ ልጇን ይዛ ከአረጋዊ ዮሴፍና ሰሎሜ ጋር በመሰደድ ግብፅ አገር የገባችበት ዕለት ነው፡፡
ግንቦት 25 ተወዳጅ ልጇ የደረቁ በትሮችን ተክሎ በተአምራት ያለመለመበት ዕለት ናቸው፡፡
በዚህ ዕለትም እናታችን፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ ለ5 ቀናት በግልጽ መታየቷ፣ የሞቱት መነሣታቸው፣ ብርሃን መሆኑ (ጨለማ መጥፋቱ)፣ የሰውን ልመና መቀበሏ …ወዘተ ይነገራል።
“ድንግል ሆይ! በሁሉ አንደበት መመስገን የተገባሽ ስለሆነ በሰማይ ካሉ መላእክትና በምድር ከሚኖሩ ደቂቀ አዳም ሁል ጊዜ ምስጋና ይቀርብልሻል።”
[ቅዳሴ ዘእግዚእትነ ማርያም]
“ሰላም ለእለ ርእዩኪ ከመ ዐይነ ወለት ኀበ እማ፣
መዋዕል ሐምስ እስከ ይትፌጸማ፣
ማርያም ንግሥት ዘደብረ ምጥማቅ ከተማ፣
ብፁዓት አዕይንት ዘነጸራኪ በግርማ፣
ወብፁዓት አእጋር ቅድሜኪ ዘቆማ።”
፤አምስት ቀናት እስኪፈጸሙ ልጅ ወደ እናቷ እንደምታይ ላዩሽ ለእነዚያ ሰላምታ ይገባል፤ የደብረ ምጥማቅ ከተማ ንግሥት ማርያም ሆይ! በግርማ ያዩሽ ዓይኖች ብፁዓን ናቸው፤ ካጠገብሽ የቆሙ እግሮችም ብፁዓን ናቸው።
[ምንጭ፡ መዝገበ ታሪክ 2 ገጽ 87፣ መድብለ ታሪክ ገጽ 383]
✍️ እንግዲህ የልዑል እግዚአብሔር ልጆች ይህ ዕለት የመላእክትና የቅዱሳን ሁሉ ንግሥት፣ የሰው ልጅ ሁሉ የደኅንነት ምክንያት የሆነችው ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ በግልጥ ተገልጣ ሕዝቡን ሁሉ በሰማያዊ ብርሃንና በደስታ የባረከችበት ዕለት ነው። ቅዱሳን አባቶቻችን ስለዚህ ታላቅ ምሥጢር በዕለቱ የሚያስተምሩንን ድንቅ መንፈሳዊ ትምህርት በጥቂቱ እንመልከት፦
፩. እውነተኛው የሰላምና የፍቅር ማእከል
በደብረ ምጥማቅ እመቤታችን ስትገለጥ ክርስቲያኑም፣ እስላሙም፣ አረማውያኑም በአንድነት ሆነው ለተከታታይ አምስት ቀናት በዐይናቸው አይተዋታል። አባቶች እንደሚያስተምሩን፤ ድንግል ማርያም የሰላም እናት ናት። እርሷ በተገለጠችበት ስፍራ ሁሉ ጥላቻ፣ መለያየትና ክፉ ነገር ይጠፋል፤ በምትኩም ፍቅር፣ አንድነትና መጽናናት ይሰፍናል። ዛሬም በቤታችንና በሀገራችን ሰላም እንዲሰፍን የእናትነቷ ጥበቃ ያስፈልገናል።
፪. ሰማይ ወደ ምድር የመጣበት ምሥጢር
በዚያች ዕለት ቅዱሳን መላእክት በማዕጠንት፣ ሰማዕታት በፈረሶቻቸው፣ ሕፃናትም በደስታ እየዘለሉ በፊቷ ሲሰግዱ ሕዝቡ ሁሉ “በሰማይ ያሉ” ይመስላቸው ነበር። አባቶች ይህንን ሲተረጉሙ፦ “ልቡን ንጹሕ ያደረገ ክርስቲያን፣ እመቤታችንን በሃይማኖትና በምግባር የሚያስባት ከሆነ፣ ሕይወቱና ቤቱ ምድራዊ ሳይሆን ሰማያዊ ይሆናል” ይሉናል።
፫. የዕንባ አባሽነቷ ሕያው ምስክር
በበዓሉ ዕለት እናትና አባቱ የሞቱበት ወይም ዘመድ የናፈቀው ሰው ሁሉ “እመቤቴ ሆይ አሳዪኝ” ብሎ ሲለምናት ቀድሞ በነበሩበት መልኩ ታሳያቸው ነበር። ይህ የሚያሳየው እመቤታችን የክርስቲያኖችን ጩኸትና ዕንባ የምታብስ፣ የተከዘውን የምታጽናና፣ ለተጨነቁት ሁሉ ፈጥና ደራሽ መሆኗን ነው።
✍️ ይህ በዓል ለሁላችንም የሚያስተምረን ታላቅ ቁም ነገር አለ፦ እመቤታችንን መውደድ ማለት እንደ እርሷ በትሕትና መኖር፣ ልብን ከክፋትና ከሽንገላ ማጽዳት፣ ለሰዎች ሁሉ መልካም ማድረግ ነው። ዛሬ በፈተናና በጭንቀት ውስጥ ያላችሁ ወገኖቼ ሁሉ፣ የደብረ ምጥማቋ እናት ዕንባችሁን አብሳ በሰማያዊ ሰላሟ ትባርካችሁ።
✍️ ድንግል ማርያም ለእኛ ለኦርቶዶክሳውያን ፤
✍️ ድንግል ማርያምን እኛ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆች የምናከብራት በምክንያት ነው። እርሷ የእግዚአብሔር እናት (ወላዲተ አምላክ ስለሆነች)፣ በድኅነት ታሪክ ውስጥ ልዩ ስፍራ ስላላት፣ በእምነትና በትሕትና ምሳሌ ስለሆነች ነው።
- ከመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ
1) “ቡርክት ነሽ”
መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለማርያም፦
“ጸጋ የተሞላብሽ ሆይ፥ ደስ ይበልሽ፤ ጌታ ካንቺ ጋር ነው።” (ሉቃስ ፩፥፳፰)
እንዲሁም ኤልሳቤጥ “ከሴቶች ሁሉ በላይ ቡርክት ነሽ፥ የማኅፀንሽም ፍሬ ቡሩክ ነው።” (ሉቃስ ፩ ፥፵ ፪)
✍️ ይህ ማርያም በእግዚአብሔር ዘንድ ልዩ ጸጋ ያገኘች መሆኗን ያሳያል።
2) “ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል”
✍️ ድንግል ማርያም እንዲህ አለች፦
“እነሆ፥ ከእንግዲህ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል።” (ሉቃስ ፩፥፵ ፰)
✍️ ስለዚህ ቅድስት ድንግል ማርያምን ማክበር የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት ፍጻሜ ነው።
3) “የጌታዬ እናት”
✍️ ቅድስት ኤልሳቤጥም እንዲህ አለች፦
“የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ ይህ ከወዴት ሆነልኝ?” (ሉቃስ ፩ ፥፵ ፫)
“ጌታ” የተባለው ክርስቶስ ነው፤ ስለዚህ ማርያም “የጌታ እናት” ተብላለች።
4) ቃል ሥጋ ሆነ
የእግዚአብሔር አብ ልጅ ከእርሷ ሥጋ ነሥቶ ሰው ሆነ፦
“ቃልም ሥጋ ሆነ፥ በእኛም አደረ።” (ዮሐ. ፩ ፥፲ ፬)
✍️ ስለዚህ ድንግል ማርያም ለአምላክ ሰው መሆን ምክንያት ሆነች።
5) ሁሉም ይታዘዙላታል
በቃና ዘገሊላ ተአምር፣ ክርስቶስ በእናቱ ምልጃ ውኃን ወደ ወይን ቀየረ።
እሷም “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ” አለች፡፡ (ዮሐ. ፪ ፥ ፭)
✍️ ይህ የድንግል ማርያምን ምልጃ እና በአማኞች መካከል ያላትን ክብር ያሳያል። - ከሊቃውንት አበው ትምህርት
1) ቅዱስ አትናቴዎስ እንዲህ ይላል፦
“ማርያም በእውነት ወላዲተ አምላክ ናት፤ ከእርሷ የተወለደው በሥጋ የተገለጠ እግዚአብሔር ነው።”
✍️ ይህ ክርስቶስ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው መሆኑን ያስረዳል።
2) ቅዱስ ቄርሎስ በኤፌሶን ጉባኤ ላይ፦
“ማርያምን ወላዲተ አምላክ ብለን እንጠራታለን፤ ምክንያቱም ከእርሷ የተወለደው በሥጋ የተገለጠ የእግዚአብሔር ቃል ነው።”
3) በኤፌሶን ጉባኤ 431 ዓ.ም. ማርያም “Theotokos፣ ወላዲተ አምላክ” መሆኗን አጽንቶ አስተማረ። ይህ የቅድስት ማርያምን ክብር ብቻ ሳይሆን የክርስቶስን ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክነትን የሚገልጽ ትምህርት ነው።
4) ቅዱስ ኤፍሬም፦
“ከአንቺ የተወለደው ቅዱስ ነው፤ አንቺም ከሴቶች ሁሉ በላይ የተከበርሽ ነሽ።” - የኦርቶዶክስ አጠቃላይ አስተምህሮ ፤ ድንግል ማርያምን የምናከብራት፦
- እግዚአብሔር ስለመረጣት
- የክርስቶስ እናት ስለሆነች
- በትሕትናና በታዛዥነት ምሳሌ ስለሆነች
- የሰማይና የምድር ንግሥት ስለሆነች
- የድኅነታችን ምክንያት ስለሆነች
ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ ለግብጻውያን ለአምስት ተከታታይ ቀናት እንደምትገለጥላቸው ሁሉ ለእኛ ለኢትዮጵያውያንም በዘወትር የሕይወት ውጣ ውረዳችን ሁሉ ተገልጣ እንደምትረዳን እናምናለን። በተለይም በአብነት ትምህርት ቤት በቆሎ ተማሪነት ያሳለፈ ሁሉ “በእንተ ስማ ለማርያም” እያለ ያደገባት በመሆኑ የእሷ ፍቅር በልቡናው ጽላት ላይ ተጽፋ ትኖራለች።
ልክ እንደዚሁ ሁሉ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርታችሁን የምትከታተሉ ውድ ተማሪዎች! ዘወትር በቃል ኪዳኗ ሥር ሆናችሁ የሚገጥሟችሁ የሕይወት ፈተናዎች ሁሉ ለድንግል ማርያም ነግራችሁ በአንዳች ሳትጨነቁ ሸክማችሁን ማራገፍ ይኖርባችኋል። እሷ “የበላኤ ሰብእ እመቤት” ከዓለም የኃጢአት ዝለት የምትታደግ አእምሮውን ለብዎውን የምታድል የእነቅዱስ ኤፍሬም፣ ቅዱስ ያሬድ፣ አባ ሕርያቆስ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፣ አፄ ዘርዓ ያዕቆብ የቅርብ ወዳጅ የሆነች ለእነሱ ምሥጢርን የገለጸች ለእኛም ትገልጻለችና “ስለዚህ ድንግል ማርያምን አክብሯት ከሥዕሏም ፊት ስገዱ…”
ስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር ። አሜን።
በዓለ ሃምሳና ተግዳሮቶቹ
ከመምህር ተፈሪ መንገሻ
ከሁሉ አስቀድመን እንኳን ለጌታችንንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ በማለት መንፈሳዊ ሰላምታችንን እናቀርባለን።
አሁን የምንገኝበት ወቅት በዓለ ሃምሳ ነው። ይህ ወቅት የሞት ኃይል የተሰበረበት፣ የሰው ልጅ ነጻነት የታወጀበትና የመቃብር ድንጋይ ተንከባሎ የሕይወት ብርሃን የበራበት ነው።
ሆኖም ግን፣ ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ወይም ለክርስቲያን ወጣቶች ይህ ወቅት ሌላ ፈተና ይዞ መጥቷል። ዓቢይ ጾምን በከፍተኛ ተጋድሎ፣ በለቅሶና በጸሎት ያሳለፉ ወጣቶች፤ ዛሬ ጾሙ ሲፈታ መንፈሳዊነታቸው አብሮ የተፈታ ይመስል በስካርና በስንፍና፣ በስውርና በግልጥ ኃጢአት ማዕበል እየተወሰዱ ያሉት በርካቶች ናቸው። በዓለ ኀምሳ የነፍስ ደስታ እንጂ የሥጋ ማድለቢያና የዲያብሎስ ፈቃድ መፈጸሚያ እንዳልሆነ ሊታወቅ ይገባል።
1.1. በዓለ ሃምሳ ምንድ ነው?
በዓለ ሃምሳ ማለት ከጌታችን ትንሣኤ ጀምሮ እስከ ጰራቅሊጦስ (የመንፈስ ቅዱስ መውረድ) ድረስ ያለው የ፶ ቀናት ታላቅ የደስታ ወቅት ነው። ቤተ ክርስቲያን በዚህ ወቅት አዳም ወደ ቀደመ ክብሩ መመለሱን ለማብሠር እንዲሁም በመንግሥተ ሰማያት ጻር ድካም የለም ስትል ጾምና ስግደት እነዳይኖር አድርጋለች።
ነገር ግን ይህ ደስታ “መንፈሳዊ” መሆኑን አንርሳ። ሐዋርያት በዚህ ወቅት በፍርሃት ተቆልፎባቸው ከነበረበት ቤት ወጥተው፣ ትንሣኤውን እያደነቁ በጸሎትና በምስጋና ይተጉ ነበር። በዓለ ሃምሳ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው። በመንግሥተ ሰማያት ደግሞ ቅድስና እንጂ ርኩሰት የለም። ነገር ግን “ጾም የለም” በሚል ሰበብ ነፍሳቸውን ለሰይጣን አሳልፈው እየሰጡ ያሉ ወጣቶች ጥቂቶች አለመሆናቸውን የሁላችንም ልባችን የሚያውቀው እውነት ነው።
መንፈሳዊ በዓላት መንፈሳዊነታችንን የምናጣባቸው ሊሆን ይገባ ነበርን?!
“ወንድሞች ሆይ፥ እናንተ ለአርነት ተጠርታችኋልና፤ ብቻ አርነታችሁ/ነጻነታችሁ ለሥጋ ምክንያትን አይስጥ፥ …. ” እንዲል ቅዱስ ጳውሎስ። (ገላ ፭፥፲፫)
1.2. በዓለ ሃምሳን እንዴት ማሳለፍ ይኖርብናል?
1.2.1. እንደማንኛውም ጊዜ ቤተ ክርስቲያን መሔድን በማዘውተር
ወጣቶች ሆይ! ጾም ሲኖር ብቻ ደጅ የምትጠኑ፣ ጾም ሲፈታ ግን ቤተ ክርስቲያንን እንደ ባዕድ አገር የምትረሱ “ወቅታዊ ክርስቲያኖች” አትሁኑ።
“ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሂድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ” (መዝ. ፻፳፩፥፩)
ያለውን የዳዊትን ቃል ትታችሁ፣ “ወደ መዝናኛ ካፌ፣ ወደ ፊልም ቤት፣ ወደ ጫት ቤት እንሂድ ወዘተ” ሲሏችሁ ደስ የሚላችሁ ከሆነ፣ እናንተ ገና የትንሣኤው ብርሃን አልተገለጸላችሁም።
ጌታችን በመጽሐፍ ቅዱስ “እስከ መጨረሻው የሚጸና እርሱ ይድናል” (ማቴ. ፲፥፳፪) እንዳለ፣ ጽናት በጾም ብቻ ሳይሆን ከጾም ውጭም ይፈተናል።
1.2.2. በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጽሙድ በመሆን
በጾመ ዓርባ ወቅት የግቢ ጉባኤ መድረኮች በአገልጋዮች ተጨናንቀው፣ መዝሙሩ ፣ ጥናቱ …. ተጠናክሮ እናያለን። ትንሣኤው ሲበሠር ግን አገልጋዩ እንደ ጢስ በኖ፣ እንደ ጉም ተኖ ይጠፋል።
በግቢ ጉባኤያችሁ ውስጥ ያላችሁ አገልግሎት በትንሣኤ ማግስት መዝለፍለፍ የለበትም። በጾም ወቅት መዘምራንና አገልጋዮች ሞልተው፣ አሁን ግን ዐውደ ምሕረቱ የሚቀዘቅዝ ከሆነ አገልግሎታችሁ ለወቅታዊ ስሜት እንጂ ለዘላለማዊው ለክርስቶስ እንዳልሆነ ማረጋገጫ ነው።
“ለሥራ ከመትጋት አትለግሙ፤ በመንፈስ የምትቃጠሉ ሁኑ፤ ለጌታ ተገዙ” (ሮሜ ፲፪፥፲፩)
የሚለውን የጳውሎስን ቃል መመሪያችሁ አድርጉ። አገልግሎት በወቅትና በጊዜ አይገደብምና።
የአገልግሎት ጽሙድነት ማለት በምቾትም በችግርም፣ በጾምም በበዓልም የማይናወጥ ጽናት ማለት ነው። “በጊዜውም አለጊዜውም ጽና” እንዲል ጳውሎስ። ፪ኛ ጢሞ ፬፥፪።
ቅዱስ እስጢፋኖስ ድንጋይ እየወረደበትም አገልግሎቱን/ ምስክርነቱን አልተወም (ሐዋ. 7)። እኛ ግን ድንጋይ ቀርቶ ለምግቡ፣ ለመጠጡ ለምቾቱ ወዘተ” ስንል አገልግሎታችንን የምንረሳ ከሆነ፣ የቆምንበት መሠረት ምንኛ የላላ ነው!
አንድ ወታደር ጦርነቱ ካበቃ በኋላ የሚዘናጋ ከሆነና ጸንቶ ካልቆመ፣ ጠላት በድል በዓሉ መሐል መጥቶ ይገድለዋል።
እኛም በጾም ሰይጣንን ድል አድርገን፣ በበዓለ ሃምሳ ብንሰንፍ፣ ሰይጣን በደስታችን መሐል መጥቶ ነፍሳችንን ይማርካታል። ከዚህ ይጠብቀን።
ስለዚህ ወጣቶች ትንሣኤው በሥራ ይገለጥ! በመንፈስ የጀመራችሁትን በዝለት አታበላሹት። (ገላ. ፫፥፫)።
1.2.3. በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን በመጓዝ
መሪ የሌለው መርከብ ወዴት ይጓዛል?!
የግቢ ጉባኤ ወጣቶች በዚህ በበዓለ ሃምሳ ወቅት ሊዘነጉት የማይገባ ታላቅ መመሪያ ቢኖር በምክረ ካህንና በፈቃደ ካህን የመመላለስ መንፈሳዊ ጥበብ ነው። የዩኒቨርሲቲ:የኮሌጅ ሕይወት በዕውቀት ባሕር ላይ እንደመጓዝ ቢሆንም፣ ያንን ባሕር ያለ መሪ (ካህን) ለመሻገር መሞከር ግን ነፍስን ለጽኑ ማዕበል አሳልፎ መስጠት ነው።
ፈቃደ/ምክረ ካህን ማለት ለአንድ ክርስቲያን ወጣት የጥበቃ አጥር ነው። አጥር ያለው ተክል እንስሳት እንደማይጎዱት ሁሉ፣ በፈቃደ ካህን የሚኖር ወጣትም የዚህ ዓለም ክፉ ፈተናዎች አያሸንፉትም። የትንሣኤው ደስታ ትርጉም የሚኖረው በካህኑ ቡራኬና መመሪያ ሲቃኝ ነው።
በጾም ወቅት ብቻ “ቀኖና ስጡኝ” እያሉ ደጅ የጠኑ፣ ዛሬ ግን ጾሙ ሲፈታ ፊታቸውን ከካህኑ አዙረው ወደ ሥጋዊ ፈቃዳቸው የሮጡ ወጣቶች፤ ሳያስተውሉት ነፍሳቸውን ለተኩላ አሳልፈው የሰጡ በጎች ናቸው!
በበዓለ ሃምሳ ወቅት “ጾም የለም” ብለው የልባቸውን ክፋት ሁሉ ሲፈጽሙ፣ ያለካህኑ ምክር ሲኖሩ፤ ጌታችን “እናንተን የሚሰማ እኔን ይሰማል፤ እናንተንም የጣለ እኔን ይጥላል” (ሉቃ. ፲፥፲፮) ብሎ የተናገረውን ቃል ራሳቸው ላይ እየፈረዱበት ነው።
በበዓለ ሃምሳ ወቅት “ጾም አበቃ” በሚል ስሜት ከካህን መራቅ ሳይሆን፣ ይልቁንም ያገኙትን መንፈሳዊ ድል ለማጽናት ወደ ካህኑ ይበልጥ መቅረብ ይኖርባቸዋል። በፈቃደ ካህን የሚጓዝ ወጣት በዓለ ሃምሳን በቅድስና የማሳለፍ ልዩ ጸጋ ይታደላል።
እነዚህ የቤተ ክርስቲያን አለኝታዎች የሆኑ ወጣቶች፣ የካህናትን ምክር እንደ ኋላ ቀርነት ሳይሆን እንደ ሰማያዊ ጥበብ ሊመለከቱት ይገባል።
ስለዚህ ወጣቶች ሆይ በዚህ የደስታ ወቅት ከሰይጣን ወጥመድ የምታመልጡት በካህን ምክር ስትጓዙ ብቻ ነው። ካህኑን መፈለግ ያለባችሁ ኃጢአት ስትሠሩ ብቻ ሳይሆን፣ ቅድስናችሁ እንዳይጎድል ጭምር መሆን አለበት።
መረሳት የሌለበት ነገር በግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ዘንድ የሚታየው አንዱ ትልቅ ተግዳሮት “ምክረ ካህንን” ከ “ንስሓ” (ከኃጢአት መታጠብና ከቀኖና) ጋር ብቻ አያይዞ መመልከት ነው።
ንስሓ ውድቀት ከተከሠተ በኋላ ነፍስን የምታክም መድኃኒት ብትሆንም፣ ምክረ ካህን ግን ውድቀት ሳይመጣ፣ ኃጢአት ሳይሠሩ፣ ነፍስ እንዳትቆስል የሚደረግ “መከላከያና ቅድመ ጥንቃቄ” ነው። ወጣቶቹ ኃጢአት ሲሠሩ ብቻ ወደ ካህን የሚሮጡ ከሆነ፣ መንፈሳዊ ሕይወታቸው ሁልጊዜ በውድቀትና በጸጸት የተሞላ ይሆናል።
እንደ ግቢ ጉባኤ ተማሪነታቸው በትምህርት፣ በጓደኝነትና በወደፊት የሕይወት አቅጣጫቸው ላይ የካህን ምክር ያስፈልጋቸዋል። ካህናት “መንፈሳዊ አባቶች” ናቸው። አባት ደግሞ ልጁ ሲበድል ብቻ ሳይሆን፣ ልጁ ትክክለኛውን መንገድ ይዞ እንዲያድግ ሁልጊዜ ምክር ይለግሰዋል።
ጠቢቡ ንጉሥ “መካሪ የሌለው ሕዝብ ይወድቃል፤ በመካሪዎች ብዛት ግን ደኅንነት ይሆናል” ብሎ እንደተናገረው (ምሳሌ 11፥14)
ውድቀት (ኃጢአት) ሳይመጣ በፊት ደኅንነትን (ድልን) ለማግኘት የመካሪ አስፈላጊነትን ይገልጻል። ወጣቶቹ በምክረ ካህን ጥላ ሥር ሲሆኑ ከውድቀት ይጠበቃሉ እንጂ ውድቀትን አይጠብቁም።
ማጠቃለያ
በዓለ ሃምሳን በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት ስንመለከተው፣ የክርስቶስ ትንሣኤ ለሰው ልጅ የሰጠው ነጻነት በኃጢአት ባርነት እንድንመላለስ ሳይሆን፣ በጽድቅ ብርሃን እንድንመላለስ መሆኑን እንረዳለን። የግቢ ጉባኤ ወጣቶች ከጾም ማግስት የሚገጥማቸውን መንፈሳዊ ዝለት አሸንፈው፣ ይህን ታላቅ ወቅት በቅድስና ሊኖሩ ይገባቸዋል።
“በነጻነት ልንኖር ክርስቶስ ነጻነት አወጣን፤ እንግዲህ ጸንታችሁ ቁሙ እንደ ገናም በባርነት ቀንበር አትያዙ።” ገላትያ ፭፥፩
ነጻ ያወጣችሁ ጌታ በነጻነቱ ያጽናችሁ፤ በነፍሳችሁ ላይ የታተመው የትንሣኤው ብርሃን ደግሞ በኃጢአት ዝገት እንዳይጠፋ በጸሎትና በምክረ ካህን ጠብቁት።
ስብሐት ለእግዚአብሔር!
