“የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሰፍራል፤ ያድናቸውማል” (መዝ. ፴፫፥፯)
በዲ/ን ፍቃደ ሥላሴ ወ/ሰንበት
“የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሰፍራል፤ ያድናቸውማል” (መዝ. ፴፫፥፯)
የተወደዳችሁ የክርስቶስ ልጆች፣ ዛሬ በዚህ ታላቅ ቀን ስለ ታላቁ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል፣ ስለ መላእክት ተፈጥሮና አገልግሎት፣ እንዲሁም ቅዱስ ሚካኤል ታላቅ ሥልጣን እንመለከታለን።
ውድ የእግዚአብሔር ልጆች በዓለም ፈተናና መከራ ውስጥ ለምንገኝ ለእኛ “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል።” የሚለውን ነቢዩ ዳዊት በመዝሙሩ የተናገረው ቃል ምንኛ የሚያጽናና ነው፡፡ ይህም ማለት ቅዱሳን መላእክት የሚከቡን፣ የሚጠብቁንና ከክፉ ሁሉ የሚያድኑን የእግዚአብሔር የታመኑ አገልጋዮች ናቸው።
መላእክት፡- የእግዚአብሔር መላእክት ብርሃናውያን ናቸው፡፡ የእግዚአብሔርን ታላቅነትና ግርማ አይተው ማወቅና መመርመር ባይቻላቸው፣ በግርማውና በእሳቱ ዙፋን ፊታቸውን በክንፎቻቸው ሸፍነው በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ ይቆማሉ፡፡ የባሕሪያቸው መገለጫ እሳት ቢሆንም በፈጣሪያቸው ፍቅር ይቃጠላሉ፡፡ አብ እሳት ነው ወልድ እሳት ነው መንፈስ ቅዱስ እሳት ነው እንዳለ የብሕንሳው ኮከብ አባ ሕሪያቆስ እሳት የሆነው እግዚአብሔር በእሳታውያን መላእክት እሳት በሆነ ምስጋናቸው ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያሉ ያመሰግኑታል፡፡ የነፋስ ባሕርይ ስላላቸው የእርሱን ፈቃድ ለመፈጸም ይፋጠናሉ፡፡ የቃሉ ድምጽፅ ለመስማትና የታዘዙበትን ለመፈጸም በሰማያዊው መንበር ፊት በትጋት የሚቆሙ፤ ምስጋናቸውን የማያቋርጡ ብርሃናውያን አገልጋዮች ናቸው፡፡ መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት ‹‹መላእክቱን ነፋሳት፣ አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል ያደርጋል” እንዳለ (መዝ. ፩፻፫፥፬) መላእክት እንደ እሳት በፍቅረ እግዚአብሔር መንደድን፣ እንደነፋስ በአገልግሎት በታዛዥነት መፋጠንንና በሰማያዊ ዝማሬ ሳያቋርጡ ፳፬ ሰዓት እያመሰገኑ መኖርን ያስተምሩናል፡፡
ክፍል አንድ፡ የመላእክት ተፈጥሮ
ውድ አንባቢ መላእክት ምንድ ናቸው? ማን ናቸው? ከየት መጡ?
1.1. መላእክት መንፈሳውያን ናቸው።
እግዚአብሔር አምላካችን ሰማይንና ምድርን በፈጠረበት ዕለት፣ የማይታዩ መንፈሳውያን ፍጥረታትን ፈጠረ፤ እነዚህም መላእክት ናቸው።
በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ መሠረት ቅዱሳን መላእክት በእግዚአብሔር ፈቃድና ቃል ካለመኖር ወደመኖር የመጡ፣ ረቂቃን፣ ብረሃናውያን፣ ፈጣሪያቸውን ለማመስገንና የሰውን ልጅ ለመጠበቅ የተፈጠሩ መንፈሳዊያን ፍጥረታት ናቸው፡፡
ቅዱሳን መላእክት ከአገልግሎታቸው አንጻር ምንድናቸው
1.2. መላእክት ረቂቃን፣ የማይሞቱ፣ ብልህና ኃያላን ናቸው።
ረቂቃን – ሥጋና ደም የላቸውም፤ መናፍስት ናቸው።
የማይሞቱ– ሞት አይነካቸውም፤ ዘላለማዊ ናቸው።
ብልህና ጥበበኞች – ከሰው በላይ የላቀ ዕውቀት አላቸው።
ኃያላን – ከሰው ኃይል የላቀ ኃይል ተሰጥቷቸዋል።
ስለዚህ ቅዱሳን መላእክት እንደሰው የሚዳሰስ ሥጋና ደም፣ ጅማትና አጥንት የሌላቸው ረቂቃንና መንፈሳዊያን ፍጥረታት እንደሆኑ ሊቁ ቅዱስ ባስልዮስ በሀይምኖተ አበው እና መጽሐፈ አክሲማሮስ (የእሑድ ፍጥረት) ላይ ‹‹መላእክት ሥጋና ደም የሌላቸው፤ረቂቃንና ብርሃናዊያን አገልጋዮች ናቸው፡፡››
ነገር ግን ልብ ልንል የሚገባን ነገር ቅድስተ ቤተ ክርስቲያን እንደምታስተምረን መላእክት ፍጡራን እንደመሆናቸው መጠን፣ ኃይላቸውም ሆነ ጥበባቸው ከፈጣሪያቸው የተሰጣቸው እንጂ የባሕሪያቸው አይደለም። እነርሱ ራሳቸው ፈጣሪ አይደሉም፤ የፈጣሪ አገልጋዮች ናቸው እንጂ።
1.3. የመላእክት ተፈጥሮ እና መዓርግ
‹‹የመላእክት ተፈጥሮ አንድጊዜ አይምሰለህ፤ በመጀመርያ ሰዓተ መዓልት ባለሟልነት ያላቸው መላእክት ተፈጠሩ፡፡ እኒህም የቅዱስ ሚካኤል ነገድ ናቸው፡፡ ይህም ነገር እውነት እንደሆነ “ከቀደሙ አላቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳን መጣ ይላል።” (ዳን. ፲፤፲፫) በሁለተኛ ሰዓተ መዓልት ምስጋና የሚያቀርቡ መላዕክት ፈጠረ፡፡ እኒህም ካህናተ ሰማይ (ኪሮቤል) ናቸው፡፡በሦስተኛ ሰዓተ ምዓልትም መናብርትን ፈጠረ፡፡ በአራተኛው ሰዓተ መዓልትም ሥልጣናትም ፈጠረ፡፡ በአምስተኛው ሰዓተ መዓልትም አጋዕዝትን ፈጠረ፡፡ በስድስተኛው ሰዓተ መዓልት ኃይላትንፈጠረ፡፡በሰባተኛው ሰዓተ መዓልትም ረበዋትን (ሊቃናት)ፈጠረ፡፡ በስምንተኛው ሰዓተ መዓልት መኳንንትን ፈጠረ፡፡ በዘጠነኛው ሰዓተ መዓልት ሁሉም መላእክት ከተፈጠሩ በኋላ ዐርባብን ፈጠረ፡፡ በአሥረኛው ሰዐተ መዓልት የአሥረኛው መዓርግ (ከተማ) መሙያ የሆኑ የዲያብሎስን ነገድ ፈጠረ››፡፡ ተብሎ ተመዝግቦ እንገኛለን፡፡ በመጽሐፈ ምሥጢር ሰማይ ወምድር (በገጽ ፰)
ቅዱሳን መላእክት ተፈጥሮአቸው ከምንም ካለመኖር ወደ መኖር ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “መላእክቱም መንፈስ አገልጋዮቹንም የእሳት ነበልባል የሚያደርግ” (መዝ. ፩፻፫፥፬) በማለት የተናገረው፡-
- እንደእሳትና ነፋስ ረቂቅ መሆናቸው፣
- ለተልዕኮ የሚፋጠኑ መሆናቸው፣
- ኃያልነታቸውንና ፈጻሚያን ፈቃድ መሆናቸውን ለመግጽ ነው እንጂ ከእሳትና ከነፋስ ተፈጥረዋል ማለት አይደለም፡፡ ቅዱሳን መላእክት ከእሳትና ከነፋስ ተፈጥረዋል ከተባለ ኃላፊያን፣ ጠፊዎችና መሬታውያን ናቸው ማለት ይሆናል፡፡ እሳትና ነፋስ ያልፋሉና። “ሶበሰ ተፈጥሩ እምነፋስ ወእሳት እመሞቱ ወእመማሰኑ እምከማነ፤ ከእሳትና ከነፋስ ተፈጥረውስ ቢሆን ኖሮ እንደኛ በሞቱ ነበር ›› በማለት አክሲማሮስ ተናግሮአል፡፡
ዓለመ መላእክትና አሰፋፈራቸው
የቅዱሳን መላእክት አሠፋፈርን በተመለከተ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ አክሲማሮስ በተባለ መጽሐፉ እግዚአብሔር መላእክትን በዕለተ እሁድ ፈጥሮ በኢዮር፣ በራማ፣ በኤረር በከተማ አሥር በነገድ ደግሞ መቶ አድርጎ እንደአሠፈራቸው ተናግሯል፡፡
ቅዱሳን መላእክት በነገድ መቶ መሆናቸውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሮአል። (ማቴ. ፲፰፥፲፪) ከመቶው አንዱ ዲያብሎስ ነበር በዲያብሎስ ፈንታም አዳም ተተክቷል “የጠፋውና የተፈለገው” አዳም ነው፡፡
በከተማ አሥር ስለ መሆናቸውም ዐሥር ድሪም ያላት ብትኖር አንዲቱ ብትጠፋባት መብራት አብርታ በቤቷ ያለውን ሁሉ እየፈነቀለች እስክታገኛት ድረስ ተግታ ትፈልግ የለምን በማለት አስረድቷል። (ሉቃ. ፲፭፥፰)
ከሰባቱ ሰማያት መካከል ሦስቱ ሰማያት ማለትም ዓለመ መላእክት የመላእክት ከተማ /መኖሪያ/ ሲሆኑ፣ እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክትን በነገድ መቶ በከተማ ዐሥር አድርጐ በሦስቱ ሰማያት በኢዮር፣ በራማና በኤረር አስፍሯቸዋል።
ክፍል ሁለት፡ የመላእክት አገልግሎት
2.1. እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ።
የቅዱሳን መላእክት ቀዳሚው አገልግሎታቸው የፈጠራቸውን አምላክ እግዚአብሔርን ማመስገን ነው። ሲያመሰግኑም “የመናፍስት ጌታ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ነህ፤ ፍጥረትህም ምድርን ይሞላል እያሉ ያከብራሉ፤ ያመስግናሉ፤ ከፍ ከፍም ያደርጋሉ።” (ሄኖክ ፱፥፴፱፣ ኢሳ. ፮፥፪-፬) እንዲሁም (ራዕ. ፬፥፲፩) ላይ እንደምናነበው “ጌታችንና አምላካችን ሆይ አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና በፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና ክብርና ውዳሴ ኃይል ላንተ ይገባል” እያሉ ያመሰግናሉ።
“አየሁም በዙፋኑ በእንስሶች በአለቆች ዙሪያ የብዙ መላእክት ድምጽ ሰማሁ ቁጥራቸውም የብዙ ብዙ እልፍ አእላፋት ነበር በታላቅ ድምጽ እንዲህ አሉ ለታረደው በግ ኃይልና ባለጠግነት ጥበብና ብርታትንም ክብርና ምስጋናንም በረከትንም ሊቀበል ይገበዋል። በሰማይና በምድር ከምድርም በታች በባሕርም ላይ ያለው ፍጥረት ሁሉ በእነርሱም ውስጥ ያለው ሁሉ በረከትና ክብር ምስጋናና ኃይልም ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም በዙፋኑ ለተቀመጠው ለበጉ ይሁን ሲሉ ሰማሁ” (ራእ. ፭፥፲፩-፲፬) እንዲል ያለማቋረጥ እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ።
2.2. ከአምላክ ወደ ሰው ይላካሉ።
መልአክ ማለት ራሱ “የተላከ” ወይም “መልእክተኛ” ማለት ነው። ይህ ስያሜያቸው ራሱ ተግባራቸውን ይገልጣል። እግዚአብሔር ከሰማይ ወደ ምድር መልእክቱን፣ ትእዛዙን፣ ተስፋውንም ለማድረስ መላእክቱን ይልካቸዋል። ቅዱሳን መላእከት ከፈጣሪ ምስጋና አገልግሎታቸው ቀጥሎ ለፍጥረቱ የሚሰጡት አገልግሎታቸው በተለይም በአዳምና በልጆቹ ጎልቶ ይታያል። ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የቅዱሳን መላእክት አግልግሎት በተመለከተ ‹‹የቅዱሳን መላእክት የሰዎችን ጸሎትና ንስሓ ወደ ፈጣሪ የሚያቀርቡ የሰላም መልእክተኞች ናቸው›› በማለት የሰውና መላእክት ጥብቅ ግኑኝነት ይገልጻል፡፡
- ገብርኤል ወደ ድንግል ማርያም ተልኮ የምስራች ብሥራት አበሠራት።
- ሚካኤል ወደ ብዙ ቅዱሳን ተልኮ ረዳቸው፤ ከእነዚህም ዳንኤል፣ ባህራን፣ አፎሚያ ይጠቀሳሉ።
- መላእክት ወደ እረኞች ተልከው የክርስቶስን ልደት አበሠሩ።
እነዚህ ሁሉ መላእክት በእግዚአብሔርና በሰው መካከል እንደ ድልድይ ሆነው እንደሚያገለግሉ ያሳዩናል።
2.3. የሰውን ልመና ወደ አምላክ ያደርሳሉ
እንደ ገና መላእክት ከላይ ወደ ታች ብቻ ሳይሆን፣ ከታች ወደ ላይም ያገለግላሉ። የሰውን ጸሎትና ልመና ተቀብለው ወደ እግዚአብሔር ዙፋን ያደርሳሉ። መጽሐፈ ኪዳን እንደሚያስተምረን፣ የቅዱሳን ጸሎትና እንባ በመላእክት እጅ እንደ ዕጣን ሆኖ ወደ እግዚአብሔር ፊት ይቀርባል።
ይህ የመላእክት ድርብ አገልግሎት – ከላይ ወደ ታች መልእክት ማድረስ፣ ከታች ወደ ላይ ልመና ማድረስ ነው። እነርሱ በእውነት የሰማይና የምድር አገናኞች ናቸው።
የቅዱሳን መላእክት አዳኝነት “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ያድናቸውማል። (መዝ. ፴፫፥፯) እዚህ ላይ መመልከት የሚገባን ነገር ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት የቅዱሳን መላእክትን አገልግሎት ሲገልጥ፡፡
1ኛ. የእግዚአብሔር መልአክ ማለቱን ቅዱስ ዳዊት ይህን ያለበት ምክንያት የእግዚአብሔር ያልሆነ ፍጥረት ኖሮ አይደለም እንደውም በ፳፫ተኛው መዝሙሩ “ለእግዚአብሔር ምድር በምልዓ ዓለምኒ ወኩሎሙ እለ የነብሩ ውስቴታ፤ ምድርና መላዋ የእግዚአብሔር ነው” በማለት የሁሉ ፈጣሪ የሁሉ አስገኝ ቅዱስ እግዚአብሔር እንደሆነ ነግሮናል፡፡ (መዝ. ፳፫፥፩) ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹ወቦቱ ኩሉ ኮነ ወዘእንበሌሁሰ አልቦ ዘኮነ፤ ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነውም አንዳች እነኳን ያለእርሱ አልሆነም” በማለት ፍጥረት ሁሉ የእግዚአበሔር ገንዘብ እንደሆነ ያረጋግጣል፡፡ (ዮሐ. ፩፥፫)
ታዲያ ክቡር ዳዊት ቅዱሳን መላእክትን ‘የእግዚአብሔር መላእክት’ በሎ የጠራቸው ከርኩሳን አጋንንት ተለይተው እግዚአበሔርን በማመስገን የእግዚአበሔርን ፈቃድ በመፈጸም ጸንተው መኖራቸውን ለመግለጥ ነው፡፡ ስለዚህ እኛ የምናከብራቸው የምንሰገድላቸው የምንማፀናቸውና በቃል ኪዳናቸው የመንታመንባቸው መላእክት የእግዚአብሔር ስለሆኑ እንጂ መላአክት በመሆናቸው ብቻ አይደለም፡፡
ርኩሳን መላእክትም በተፈጥሮአቸው መላእክት ቢሆኑም ከእግዚአብሔር ስለተለዩ እግዚአብሔርንም ስለማያመሰግኑ እኛም አንወዳቸውም ይልቁንም እንረግማቸዋለን እንጂ፡፡ በጸሎታችንም መጀመሪያ ላይ “በቅድስት ሥላሴ እያመንኩ እና እየተማፀንኩ ጠላቴ ሰየጣንን እክድሃለሁ፤ በዚህች በእናቴ ቤተክርስቲያን ፊት ቆሜ እክድሃልሁ፤ ለዚህም ምስክሬ ማርያም ናት›› በማለት ዲያበሎስንና ሠራዊቱን እንረግማቸዋለን።
2ኛ. በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ የሠፍራል በማለት እግዚአብሔርን በሚፈሩ ሰዎች ዙሪያ የእግዚአበሔር መልአክ የሚገኝ መሆኑን ያስረዳል፡፡ ጌታችን መድኃኔ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል ‹‹ከእነዚህ ከታናናሾቹ አንዱን እንዳትንቁ ተጠንቀቁ፤ መላእክቶቻቸው በሰማያት ዘወትር የአባቴን ፊት ያያሉና›› (ማቴ. ፲፰፥፲) እንዳለ ቅዱሳን መላእክት ዘወትር ከእግዚአብሔር ሕዝብ አይለዩም፡፡
3ኛ ያድናቸውማል በማለት የቅዱሳን መላእክትን አዳኝነት ያረጋግጣል አዳኝ በመሆናቸው ላይ እስራኤልን ከፈርኦናውያን ማዳናቸው (ዘጸ. ፲፬፥፲፱) ሠለስቱ ደቂቅንና ዳንኤልን ከእሳትና ከአንበሳ (ዳን. ፫፥፳፭፤ ፮፥፳፪) ቅዱስ ጴጥሮስን በእስር ቤት እንደጠበቀው እንመለከታለን። (ሐዋ. ፲፪፥፲፩)
ክፍል ሦስት፡ የቅዱስ ሚካኤል ሥልጣን
3.1. በመላእክት ዘንድ
ቅዱስ ሚካኤል የዘጠኙ መዓርጋተ መላእክት ሁሉ አለቃ ነው። ስሙ ራሱ “ሚካኤል” ማለትም “ማን እንደ እግዚአብሔር” ማለት ነው። ስያሜውም ያገኘበት ደግሞ ትልቅ ታሪካዊ ምክንያት አለው።
ትውፊታችን እንደሚያስተምረን፣ በመፅሐፍ ቅዱስ ተጠቅሶም እንደምናገኘው (ኢሳ. ፲፬፥፲፪፣ ራእ. ፲፪፥፯) ሳጥናኤል (ዲያብሎስ) ገና ከክብሩ ሳይወድቅ በፊት፣ “እኔ በእግዚአብሔር ዙፋን ላይ ልቀመጥ ነው፣ ራሴንም ከልዑል አስተካክላለሁ” ብሎ ትዕቢት ባሰበ ጊዜ፣ ቅዱስ ሚካኤል የመላእክትን ሠራዊት አስከትሎ “ማን እንደ እግዚአብሔር” እያለ ተጋደለው። በዚህም ድል በማድረጉ “ሚካኤል” የሚለው ስም ተሰጠው። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በመላእክት ዘንድ ታላቅ አለቃና መሪ ተብሎ ተሾመ።
3.2. በዲያብሎስ ዘንድ
ቅዱስ ሚካኤል በዲያብሎስና በአጋንንት ላይ ትልቅ ሥልጣን ተሰጥቶታል። ይህንን እውነታ በዘመነ ብሉይና በዘመነ ሐዲስ በቅዱሳት መጻሕፍት ተመዝግቦ እናገኛለን፡፡ ቅዱስ ይሁዳ በመልእክቱ ላይ ይመሰክራል፡- ስለ ሙሴ ሥጋ ከሰይጣን ጋር ተከራክሮ እንደነበር ይናገራል። ይህ ትንሽ ታሪክ ቢመስልም፣ ቅዱስ ሚካኤል በዲያብሎስ ላይ ያለውን ልዕልናና ኃይል ያሳየናል። ዲያብሎስና ሠራዊቱን በኃይለ መስቀሉ ያሸነፈ፣ ሰይጣን ስሙን ሲሰማ የሚንቀጠቀጥለት የብርሃን መልአክ ነው።
ዛሬም ድረስ ኦርቶዶክሳዊያን ከክፉ መንፈስ፣ ከዲያብሎስ ተንኮል ለመጠበቅ በቅዱስ ሚካኤል ስም ጸሎት ያደርጋሉ፤ ምክንያቱም እርሱ በእግዚአብሔር የተሰጠው ሥልጣን በዲያብሎስና በሠራዊቱ ላይ ትልቅ ኃይል ስላለው ነው።
ክፍል አራት፡ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስን እንደረዳው
ቅዱስ ሚካኤል በዘመናት ሁሉ ለቅዱሳን ብቻ ሳይሆን ለነገሥታትም ረዳት ሆኖ ኖሯል። ከእነዚህ ታላላቅ ታሪኮች አንዱ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስን የረዳበት ታሪክ ነው።
4.1. ጠላቶቹን በትዕምርተ መስቀል እንደጣለለት
ውድ ወገኖቼ፣ በ፫፻፲፪ ዓ.ም ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ከጠላቱ ከመክስምያኖስ ልጅ ማክሰንጥዮስ (Maxentius) ጋር ትልቅ ጦርነት ሊገጥም ተዘጋጅቶ ነበር፤ ቆስጠንጢኖስ ከጠላቱ ማክሰንጥዮስ ጋር በሚልቪያን ድልዲ የጦር ሜዳ ላይ ከመሰለፉ በፊት ያየውን ታላቅ ምልክት በትውፊት መነጽር ስንመለከተው፡፡
የቤተክርስቲያን ታሪከ ጸሐፊው አውሳብዮስ ዘቂሳሪያ በጻፈው (Life of Constantine) ጽሑፍ ውስጥ እንደሚተርከው ቆስጠንጢኖስ ከጦርነቱ በፊት በሰማይ የመስቀል ምልክት እንዳየና ‹‹በዚህ ምልክት ድል ታደርጋለህ›› የሚል እንደነበረ ይናገራል፡፡ ይህን ምልክት ባየ ጊዜ የመስቀሉ ምልክት በሰንደቅና በጦር መሳሪያዎች ላይ እንዲያስቀምጡ ለወታደሮቹ እንዳዘዘ ይናገራል፡፡
ለዓለም የውርደትና የሞኝነት ምልክት የመሰለው መስቀል (፩ቆሮ. ፩፥፲፰) ለክርስቲያኖች የድል፤ የመዳን፤ የድልና የክርስቶስ ኃይል ሆኖ አየነው፡፡
የሜላን አዋጅ (Edict of Milan) ቤተክርስቲያንን ከምድር ውጭ ወይም ከዋሻና ከካታኮምብ (Catacombs) አውጥቶ በዓለም መድረክ ላይ በግልጽ እንድትበራ ያደረገ ታሪካዊ መምሪያ ነው። ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ በትዕምርተ መስቀሉና በቅዱስ ሚካኤል ረዳትነት ያገኘውን ድል ወደ ሕግና ነጻነት በመቀየር፣ ለቤተክርስቲያን ወርቃማ ዘመን (Golden Age of the Church) መጀመር ዋናው ምክንያት ሆኗል።
ሰማያት ፈጣሪያቸው ያመሰግናሉ፤ ምድረም ትዘምራለች፤ ቤተክርስቲያን ከሰማያዊ ኃይላት ጋር አንድ ሆና ትቀድሳለች፡፡ ስለዚህ ስለ መላእክት ማወቅ የማይታየውን ዓለም ማወቅ ብቻ ሳይሆን፤ የእግዚአብሔር ታላቅ ጥበብ፣ ክብርና ፍቅር በጥልቀት መረዳትም ጭምር ነው፡፡
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን።
