“እናቴ ሆይ ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ”

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ላይ ተመሥርታለችና ዙሪያዋን በከበቧት ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን መላእክት፣ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ተጋድሎና ጸሎት የታጠረች ናት፡፡ “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤ በተራራ ላይ የተሠራች ከተማ መሰወር አይቻላትም” (ማቴ. ፭፥፲፬) እንዲል መጽሐፍ ቅዱስ ቅዱሳንን በብርሃን ይመስላቸዋል፤ ቅዱሳን ወንጌልን በመስበክ ዓለምን አጣፍጠዋታልና፡፡

ቤተ ክርስቲያን ለእነዚህ ዓለምን ድል ለነሱ ቅዱሳን ከዓመት እስከ ዓመት የተወለዱበትን፣ ተአምራት ያደረጉበትንና ያረፉበትን ቀን አስልታ መታሰቢያቸውን በድምቀት ታከብራለች፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት መካከል ደግሞ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ንጉሡ ለሚያመልከው ጣኦት አንሰግድም በማለታቸው መከራ የተቀበሉበትና በእምነታቸው ጽናት እግዚአብሔርን ደስ በማሰኘታቸው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከነደደው እሳትና የፍላቱ ኃይል ዐሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደ ላይ ከሚዘል የፈላ ውኃ ያዳነበትን ቀን ሐምሌ ፲፱ ቀን አስባ በድምቀት ታከብራለች፡፡

በቤተ ክርስቲያን በየዕለቱ ከሚነበቡ መጻሕፍት መካከልም ስንክሳር ታሪኩን እንዲህ ይተርከዋል፡፡

ቅድስት ኢየሉጣ በሮም ግዛት በሚገኝ አንጌቤን በሚባል አገር በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በክርስትና ሃይማኖት እና በበጎ ምግባር ጸንታ ትኖር የነበረች ደግ ሴት ናት፡፡ በሥርዓት ያሳደገችው ቂርቆስ የሚባል የሦስት ዓመት ሕፃን ልጅም ነበራት፡፡ ይህቺ ቅድስት የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራቷ ከልጇ ጋር ከሮም ወደ ጠርሴስ በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡

የንጉሡ ወታደሮችም እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን አስፈራሯቸው፡፡ ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኃ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡

በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡

አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም “እናቴ ሆይ! ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ” እያለ ቅዱስ ቂርቆስ እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን እንድትጸና አበረታታት፡፡ የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡ እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አስነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲሆን፣ መኰንኑ በተአምራቱ ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡

ዳግመኛም በፈላ የጋን ውኃ ውስጥ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ፤አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ ከፈላ

 ውኃ ያድነናል እያለ ያረጋጋት፣ በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡

ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ውኃውን እንደ ውርጭ አቀዘቀዘው፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ አስገብተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል አድኗቸዋል፡፡ በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡

እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ እያለ በእሳት ውስጥ ሊጣሉ ባሉበት ወቅት እናቱን እንድትጸናና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ሁሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል አይዞህ! አይዞሽ! አትፍራ! አትፍሪ በመባባል በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ ታግሠን፣ እስከ ሞት ድረስ በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር ይገባናል፡፡

ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይሆን በጋራ ዋጋ የሚያገኙበት የድኅነት በር ነውና፡፡ ከዚሁ ሁሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን በተአምኖ ንሴፎ ትንባሌ ዚአከ መዓልተ ወሌሊተ፤ በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡ እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል” ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፴፬፥፯)፡፡ ይህን እንድናደርግም የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡ የቅዱስ ገብርኤል፣ ቅድስት ኢየሉጣ እና ቅዱስ ቂርቆስ ጸሎታቸውና ምልጃቸው ይጠብቀን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ

“ዓላማዬ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችን በዕውቀት ማነጽ ነው” (ሄኖክ ግዛው)

ሄኖክ ግዛው በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የ፳፻፲፯ ዓ.ም ተመራቂ ነው፡፡ በሒሳብ ትምህርት ክፍል አጠቃላይ ውጤት የትምህርት ክፍሉ ሜዳልያና በዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ ውጤት ደግሞ 3.99 በማስመዝገብ በከፍተኛ ውጤት የዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል፡፡ ዩኒቨርሲቲውም በመደበኛ መምህርነት በመቅጥር የሁለተኛ ዲግሪውንም ስፖንሰር በማድረግ እንዲማር ዕደል ሰጥቶታል፡፡

ሄኖክ ይህንን ውጤት እንዴት ማምጣት ቻለ? የቤተሰቦቹና የመምህራኑ ድርሻ ምን ነበር? አስተዳደጉና ለትምህርት የሰጠውን ትኩረት አስመልክተን ከዝግጅት ክፍላችን ጋር ቆይታ አድርጓል፡፡ እንዲህ ተዘጋጅቷል፡፡

ስለ አስተዳደግህ በመግለጽ ውይይታችንን ብንጀምር?

ሄኖክ፡- የተወለድኩት ከወልቂጤ ከተማ 42 ኪሎ ሜትር ርቀት በምትገኘውና ከአበሽጌ ወረዳ ወጣ ብላ በምትገኝ በምዕራብ ሸዋ ዞን ገጠር ቀበሌ ውስጥ ነው፡፡ እንደማንኛውም የገጠር ልጅ ለቤተሰብ እየታዘዝኩ፣ ከብቶች እየጠበቅሁና እያሰማራሁ ነው እስከ ዘጠኝ ዓመቴ ያደግሁት፡፡ ትምህርቴንም በሚመለከት አባቴ እስከ ስምንተኛ ክፍል ተምሮ የነበረ ቢሆንም ቤተሰብን ለመርዳትና ራሱንም ለመቻል ወደ ግብርናው ተሰማርቶና ትዳር ይዞ ኖረ፡፡ ነገር ግን ከፍተኛ ቁጭት ስለነበረው የትምህርት እልሁን በእኛ በልጆቹ መወጣት ይፈልግ ነበር፡፡ በአካባቢያችን ጥሩ ትምህርት ቤት ስላልነበረ ታላቅ ወንድሜን አስቀድሞ ወደ ወደ አበሽጌ ከተማ ልኮ ያስተምረው ስለነበር እኔንም ከወንድሜ ጋር ትምህርቴን እንድከታተል ወደ አበሽጌ ላከኝ፡፡ በየሳምንቱ ዓርብ ለሳምንት የሚሆነን ምግብ ይላክልናል፤ የእኛ ድርሻ መማር ብቻ ነበር፡፡

ለትምህርት የነበረህ ፍላጎትና ውጤትህ ቤተሰቦችህ ላይ ያሳደረው ተጽዕኖ አልነበረም?

ሄኖክ፡- ለታናናሾቼ አርአያ ሆኛለሁ ማለት እችላለሁ፤ እኔን ተከትለው እነርሱም ከፍተኛ የትምህርት ፍቅር አላቸው፡፡ እኔ ደግሞ የታላቅ ወንድሜ ውጤታማነት አግዞኛል፤ እኔም በተፈጥሮ የነገሩኝን ነገር ያለመርሳት፣ በትምህርቴም ክፍል ውስጥ አስተማሪዎቼ ሲያስረዱ የመቀበል አቅም ነበረኝ፡፡ በውጤቴም እስከ መጨረሻው ድረስ የደረጃ ተማሪ ነበርኩ፡፡ ስምንተኛ ክፍልንም 100 ውጤት አምጥቼ ዘጠነኛ ክፍልን ለመማር ወደ ወልቂጤ ከተማ መጣሁ፡፡ ወልቂጤም ብዙ አልተቸገርኩም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ተከታትዬ በጥሩ ውጤት ነው ያለፍኩት፡፡ እናትና አባቴ አንዲት እኅትና አራት ወንድ ልጆችን ነው የወለዱት፡፡ ታላቅ ወንድሜ ከኮሌጅ ተመርቆ አዲስ አባባ ሥራ ላይ ነው፣ እኔ እግዚአብሔር ፈቅዶ ዘንድሮ ተመርቄያለሁ፣ ታናሽ ወንድሜ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሦስተኛ ዓመት አርክቴክቸር ተማሪ ሲሆን ትንሹም በትምህርት ላይ ይገኛል፡፡ አንዲት ታላቅ እኅት ነበረችን እርሷም ትታመም ስለነበር ጸበል በሄደችበት ነው ያረፈችውና ከባድ ኀዘን ነበር በቤታችን ውስጥ የተፈጠረው፡፡

ከቤተሰቦቼ ጋር በጣም የጠበቀ ቅርበት ስለነበረኝ አቅማቸው በፈቀደ መጠን ከማበረታታት ወደኋላ አላሉም፡፡ በተለይ አባታችን ተምራችሁ አንድ ደረጃ ላይ መድረስ አለባችሁ እያለ ስለሚመክረን የቅርብ ክትትሉ አልተለየንም፡፡   

በሰንበት ትምህርት ቤት ስለነበረህ ተሳትፎ ብትገልጽልን? 

ሄኖክ፡- ቤተ ክርስቲያን ከጓደኞቼ ጋር እሄዳለሁ፣ በሰንበት ትምህርት ቤትም በአባልነት ወጣ ገባ ያለ ተሳትፎ ብቻ ነበር የነበረኝ፡፡ እንደ ወጣት ዓለም ስባ እንድታስቀረኝ ዕድሉን አልሰጠኋትም፤ እምነቴን ለመጠበቅ ጥረት እያደረግሁ ነው ያደግሁት፡፡ መውደቅ መነሣቱ ቢኖርም በእምነት ጸንቼ ለመኖር የምችለውን ሁሉ ሳደርግ ነበር፡፡ ወደ አገልግሎት የመግባት ዕድሉን ግን አላገኘሁም፡፡ በተፈጥሮ ዝምታን ስለማበዛ ራሴን ለመማር እንጂ ለማገልገል አላዘጋጀሁትም፡፡  

ከፍተኛ ትምህርት ተቋም (ዩኒቨርሲቲ) ስትገባ መንፈሳዊ ሕይወትህን እንዴት ትመራ ነበር?

ሄኖክ፡- በግቢ ጉባኤ ውስጥ በአባልነት ስሳተፍ ነበር፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ መጸለይ አዘወትራለሁ፡፡ አገልግሎትን በተመለከተ ግን ኮርስ መከታተልና በልዩ ዝግጅት ከመሳተፍ ውጪ ወደ አገልግሎት አልገባሁም፡፡

ቤተሰብ ውጤታማ ሆነህ እንድትወጣ ከመጓጓትና ለትምህርትህ ልዩ ትኩረት እንድትሰጥ ከመፈለግ አንጻር ወደ ግቢ ጉባኤ እንዳትሄድ አልተከለከልክም?

ሄኖክ፡- ቤተሰቦቼ ለትምህርት ልዩ ትኩረት እንደምሰጥ ስለሚያውቁ ወደ ቤተ ክርስቲንና ግቢ ጉባኤ እንዳልገባ ያደረጉት ጫና አልነበረም፡፡ እኔም ይህንን ስለምረዳ መቼ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ መቼ ግቢ ጉባኤ መሄድ እንዳለብኝ ስለማውቅ ሁሉንም አጣጥሜ ለመጓዝ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡

የትምህርት ክፍሌ (የሒሳብ ትምህርት) ልዩ ትኩረት የሚሻ የትምህርት ዓይነት በመሆኑ ከመምህራን ከማገኘው ዕውቀት በተጨማሪ በራሴም ከፍተኛ ጥረት ሳደርግ ነበር፡፡ የመምህራኖቼም ጥሩ ድጋፍና አይዞህ ባይነት አልተለየኝም ነበር፡፡    

የውጤታማነትህ ምሥጢር ምንድነው?

ሄኖክ፡- የመጀመሪያው ውሳኔ ነው፡፡ በዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ ከተሰጡት 50 የትምህርት ዓይነቶች 43A+ ነውያመጣሁት፣ ከአንድ ትምህርት A-ውጪቀሪዎቹ A ነው ያስመዘገብኩት፡፡ማንኛውም ቤተሰብ ልጆቹ ተምረው ዶክተር እንዲሆኑ ነው የሚመኘው፡፡ ልጆችም ብንሆን ከልጅነት ጀምሮ ዶክተር ወይም አውሮፕላን አብራሪ እንድንሆን እንመኛለን፡፡ እኔ ግን መምህርነትን ከልጅነቴ ጀምሮ ነው ስመኘው የኖርኩት፤ ቤተሰብም ሲጠይቀኝ መምህር ነው የምሆነው ስለምላቸው በውሳኔዬ ነው የጸናሁት፡፡ የመጀመሪያ ዓመት ውጤቴም ከፍተኛ ስለነበረ ለምን ሕክምና አታጠናም የሚሉኝ ብዙዎች ነበሩ፡፡ እኔ ግን ፍላጎቴ ስላልነበር ተማሪዎች የትምህርት ክፍላቸውን ሲመርጡ እኔ ግን ሐሳቤን እንዳልቀይር ግቢውን ትቼ በመውጣት ወደ ቤተ ክርስቲያን ነው የሄድኩት፡፡ 

ከግቢው ከፍተኛ ውጤት ማምጣት አለብኝ ብዬ አልነበረም የማጠናው፡፡ ነገር ግን በሂደት ጥሩ ውጤት እያመጣሁ መሆኔን ስረዳ ነው በጥሩ ውጤት ተመርቆ የመውጣት ፍላጎቴ ከፍ ያለውና ቢያንስ ሜዳልያ ማግኘት አለብኝ የሚለው ፍላጎት ያደረብኝ፡፡ የጓደኛ ግፊት፣ ሌሎች ሱሶች የሚያጠቁኝ ሰው አይደለሁም፤ ከዓላማዬ የሚያዘናጋኝም የተለየ ችግር ስላልነበር ሙሉ ትኩረቴን ትምህርቴ ላይ ነበር የማሳርፈው፡፡ 

ፈተና ሲኖርም ጠለቅ ያለ ጥናቴን በሦስት ቀን ውስጥ አጠናቅቃለሁ፤ ክፍል ውስጥ የሚሰጠውን ትምህርት በትኩረት እከታተላለሁ፤ አንድ ጊዜ ከተረዳሁ ደግሞ አልረሳም፣ በዚህ ላይ የሒሳብ ትምህርት ክፍል መምህራኖቼ ድጋፍ ስለማይለየኝ በውጤት መዋዠቅ ውስጥ ሳልገባ እስከ መጨረሻው መዝለቅ ችያለሁ፡፡ 

ለጥናት የትኛውን ጊዜ ትመርጥ ነበር?

ሄኖክ፡- ከሰኞ እስከ ዓርብ ጠዋትና ከሰዓት በኋላ ትምህርት ስለሚኖረን ለጥናት ያለኝ ጊዜ ማታ ነው፡፡ ስለዚህ ከራት በኋላ ያለውን ጊዜ ነው የምጠቀመው፡፡ ራት ከበላሁ በኋላ ቢበዛ እስከ ሌሊቱ ሰባትና ስምንት ሰዓት እያጠናሁ ልቆይ እችላለሁ፡፡ ይህ ሰዓት ለእኔ ልዩ ምቾት የሚሰጠኝ ጊዜ ነው፡፡  

ጊዜህን ለትምህርትህ እንደሰጠህ ሁሉ በትርፍ ሰዓትህ በምን ትዝናና ነበር?

ሄኖክ፡- ትርፍ ሰዓት ሲኖረኝ ቀድሞ ሙዚቃ ነበር የማደምጠው ግቢ ከገባሁ በኋላ ግን ከቀድሞ ይልቅ ይበልጥ ቤተ ክርስቲያንን እያወቅኋት በመምጣቴ መዝሙር በመስማት፣ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ነው የማሳልፈው፡፡

በትምህርትህ ውጤታማ እንድትሆን የቤተሰብ ድጋፍ እንዴት ነበር?

ሄኖክ፡- ቤተሰቦቼ በመካከለኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ ናቸው፡፡ ገንዘብም ቢሆን የሚያስፈልገኝን ሁሉ በማሟላት ሲደጉሙኝ ቆይተዋል፡፡ አባቴ ለትምህርት ከተባለ ያለምንም ቅሬታ የቻለውን መሥዋዕትነት ይከፍላል፣ የጠየቅነውን ሳያሟላ ዕረፍት አይኖረውም፡፡ ስለዚህ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ውስጥ ሆኜ ቤተሰቦቼ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ አላሉም፡፡ እኔም አደራቸውን ለመወጣት የቻልኩትን ሁሉ ለማድረግ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡   

አባቴ ለትምህርት ያለው ፍቅር ከፍተኛ ስለሆነና እርሱ ያጣውን በልጆቹ መበቀል ስለሚፈልግ “ከእኔ ምንም አትጠብቁ፣ የማወርሳችሁም ነገር የለኝም፤ ስለዚህ ጠንክራችሁ ተማሩ” በማለት ከፍተኛ ግፊት ስለሚያደርግ ለትምህርት ከሆነ ማንኛውንም መሥዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ የሆነ ቆራጥ አባት ነበር፡፡ ወላጅ እናቴም ከአባቴ የተለየ አመለካከት አልነበራትም፡፡ ለራሳቸው እያስፈለጋቸው አጉድለው ለእኛ ለልጆቻቸው የሚያደረጉት ነገር ያስገርመኛል፡፡ ሁል ጊዜም ከራሳቸው ይልቅ እኛን ያስቀድማሉ፡፡ እዚህ ደረጃ ላይ ለመድረሴ የወላጆቼ ክትትልና ድጋፍ ከፍተኛ ድርሻ ነበረው፡፡

በግቢ ቆይታህ ከጓደኞችህ ጋር ምን ዓይነት ግንኙነት ነበረህ?

ሄኖክ፡- እኔ ጓደኛ ከማያበዙት ወገን ነኝ፡፡ በማደሪያ ክፍላችን ውስጥ አብረን ስላለን አንዳንድ ነገሮችን ልንነጋገር፣ ልንደጋገፍ እንችላለን፡፡ ያ ግንኙነት ጓደኝነት ነው ማለት አይደለም፡፡ ክፍል ውስጥም እንዲሁ፡፡ ነገር ግን ትምህርቴን ጨርሼ ከግቢ እስክወጣ ድረስ አንድ ጓደኛ ብቻ ነበረኝ፡፡ ከእርሱም ጋር ትርፍ ሰዓት ካለን ነው የምንገናኘው፤ በተለይ ቅዳሜ ከቅዳሴ በኋላ ጊዜ ስለሚኖረን አብረን እንሆናለን፣ ሻይ ቡና እንላለን፡፡ በግል ሕይወታችን ዙሪያም እንመካከራለን፡፡ በተረፈ ቀሪውን ሰዓት ደግሞ ዕረፍት አደርጋለሁ፡፡

ከክፍል ልጆች ጋር ደግሞ ፈተና ከመድረሱ በፊት አስረዳን ስለሚሉኝ ባዶ ክፍል ፈልገን አስረዳቸዋለሁ፣ እኔም እያስረዳሁ አብሬ እማር ነበር ማለት እችላለሁ፡፡

በግቢ የነበረህ ቆይታ በድል ተወጥተኸዋልና የወደፊት ዓላማህ ምንድነው?

ሄኖክ፡- ተቋሙ የመምህርነት ዕድሉን ሰጥቶኛል፣ በዚህ ላይ ደግሞ ሁለተኛ ዲግሪዬን እንድማር ስፖንሰር ሆኖኛል፡፡ የወደፊት ዕቅዴ በመምህርነቱ የመቀጠል ፍላጎት ቢኖረኝም ግቢ ውስጥ ለረጅም ጊዜ የመቆየት ፍላጎት የለኝም፡፡ ከታች ወርጄ አንደኛ ወይም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ ለማስተማር ነው የማስበው፡፡ ዓላማዬ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችን በዕውቀት ማናጽ ነው፤የትምህርት መሠረት የሚገነባው ከሕፃንነት ጀምሮ ነውና ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ የድርሻዬን መወጣት አለብኝ፡፡ በማኅበረሰብ አገልግሎትም የመሳተፍ ፍላጎት ስላለኝ ይህንን ሕልሜን ለማሳካት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ ልጆቹን መንገድ ማሳየት፣ መምራት ላይ ትኩረት አደርጋለሁ፡፡ እዚሁ ወልቂጤ እያስተማርኩም ታናናሽ ሁለቱን ወንድሞቼን ማስተማር፣ አብሬአቸው መኖርና ውጤታማ ይሆኑ ዘንድ መርዳት እንዳለብኝ ራሴን አሳምኜዋለሁ፡፡

በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እና በመንፈሳዊ ሕይወት ጸንቶ ለመኖር የምታደርገው ጥረት ምን ይመስላል?

ሄኖክ፡- ከልጅነቴ ጀምሮ ከተሳታፊነት ባለፈ ደፍሮ ወደ አገልግሎት የመግባት ልምዱ የለኝም፡፡ ጸጋውም ያለኝ አይመስለኝም፡፡ ነገር ግን ያለ መንፈሳዊ ሕይወት ትርጉም አይኖረውምና ጥሩ ክርስቲያን መሆን፣ ቤተሰቤንም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ተገንዝበው በመልካም መንገድ ላይ እንዲጓዙ አርአያ መሆን እፈልጋለሁ፡፡

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ተማሪዎች በመደበኛ ትምህርታቸውም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ ከተሞክሮህ በመነሣት ልምድህን ብታካፍል?

ሄኖክ፡- የገጠር ወይም የከተማ ልጅ ብሎ መከፋፈሉ አስፈላጊ ባይሆንም እስከሚለምዱት ድረስ ጫናው በገጠር ልጆች ላይ የሚበረታ ይመስለኛል፡፡ እኔም የተገኘሁት ከገጠር ስለሆነ ስሜታቸውን እጋራለሁ፡፡ ማንኛውም ተማሪ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሲገባ ግር ሊለው ይችላል፡፡ የመደናገጥ፣ ፍርሃት ውስጥ የመግባት ችግር ሊገጥመው ይችላል፡፡ ነገር ግን ይህንን በመቋቋም ከማንም እንደማያንስና የተሻለ ብቃት እንዳለው በማመን ተስፋ ሳይቆርጥ መማር ይገባዋል፡፡

ትምህርት ጊዜን ይፈልጋል፣ ለፈተና ብቻ ብለን የምናጠናው ሳይሆን ዕውቀታችን ለማስፋት፣ ወደፊት ለሚጠብቀን የሕይወት ምዕራፍ እንደሚረዳን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ከማኅበራዊ ሚዲያ ጋር ያላቸውን ቁርኝት መቀነስ፣ ሞባይላቸውን ለትምህርት አጋዥ ለሚሆኑ አገልግሎቶች ብቻ ማዋል ይጠበቅባቸዋል፡፡ ማኅበራዊ ሚዲያው ብዙዎችን ከዓላማቸው እያዘናጋ ያሰቡበት እንዳይደርሱ እንቅፋት ስለሚሆን ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ተሞክሮህን ስላካፈልከን በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ሄኖክ፡- እኔም አመሰግናለሁ፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ማስታወቂያ

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ አገልግሎቱን በማጠናከር በግቢ ጉባኤያት ላይ ውጤታማ ሥራ ለመሥራትና ብቁ አገልጋዮችን ለማፍራት ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ ፕሮጀክቶቹን ለማስፈጸም ይረዳውም ዘንድ ልዩ የገቢ ማሰባሰቢያ ትኬት ሽያጭ ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በማሠራጨት ላይ ይገኛል፡፡ እርስዎም ትኬቱን በመግዛት ትውልድን ለመቅረጽ በሚደረገው ጥረት ውስጥ አሻራዎን ያኑሩ፡፡

ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወቅዱስ ጳውሎስ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርታ የሚነበበውን ምንባብ፣ የሚዘመን ዜማ በቀለም ለይታ ሐምሌ ፭ ቀን ከዋዜማው ጀምሮ በታላቅ ድምቀት በዓላቸውን ከምታከብላቸው ሐዋርያት መካከል የሊቀ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ ዕረፍት አንዱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በምድር ላይ ሳሉ እግዚአብሔርን አምነው፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ቃል አስገዝተው ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ድውያንን እየፈወሱ፣ በየደረሱበት ቃለ እግዚአብሔርን ለተራቡና ለተጠሙ ምእመናን በመመገብና በማጠጣት በሚታወቁ ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን የተከበበች ናት፡፡ ታሪካቸውንም ሰንዳ ለትውልድ በማስተላለፍ ብቸኛዋ ተቋም ናት፡፡ 

የሐዋርያትን ታሪክ ለማወቅ ዋናው ምንጩ የቤተ ክርስቲያን የታሪክ መጻሕፍት ናቸው። በዚህም መሠረት በቤተ ክርስቲያናችን ሐምሌ ፭ ቀን በዓላቸውን ከምታከብርላቸው ሐዋርያት መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ታሪክ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በገሊላ ቤተ ሳይዳ ሲሆን እናቱ ባወጣችለት ስም ስምኦን እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ በጐልማሳነቱ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ተሠማራ። በ፶፭ ዓመት ዕድሜውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዝሙርነት ጠርቶታል፡፡ “በገሊላ ባሕር ዳር ሲመላለስም ሁለቱን ወንድማማቾች ጴጥሮስንና እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ዓሣ አጥማጆች ነበሩና ጌታችን ኢየሱስም ‘ኑ ተከተሉኝ፤ ሰውን የምታጠምዱ እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፬፥፲፰-፳) መረባቸውንም ትተው ተከተሉት፡፡ ቅዱስ ጰጥሮስ በዚህ መንገድ ነው የተጠራውና ቤተሰቡንና ያለውን ሁሉ ትቶ ጌታችንን የተከተለው፡፡

በቂሳርያ ከተማ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን “እናንተስማን ትሉኛላችሁ? ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ ብፁዕ ነህ፤ በሰማይ ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና፡፡ እኔም እልሃለሁ፡- አንተ ዐለት ነህ፤ በዚያች ዐለት ላይም ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲዖል በሮች አይበረቱባትም” አለው፡፡ ጴጥሮስ የሚለው ስም በላቲን ቋንቋ ዐለት ማለት ነው፤ በአርማይክ ደግሞ ኬፋ ይባላል። (ማቴ. ፲፮፥፲፮) በዐለት ላይ የተመሠረተ ቤት ንፋስ በነፈሰ ጊዜ እንደማይፈርስ ሁሉ በክርስቶስ የተመሠረተችው ቤተ ክርስቲያንም በንፋስ የተመሰለው ዲያብሎስ ዙሪዋን ቢዞርም ለያጠፋት እንደማይችል ያመለክታል፡፡ 

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥብርያዶስ ባሕር ላይ በእግሩ ሲራመድ ተመልክቶ እርሱም ይሄድ ዘንድ ፈቃድ የጠየቀ፣ መሄድ የጀመረና ማዕበሉን ፈርቶም የተጠራጠረ፣ በዚህም ምክንያት ለመስጠም የደረሰ፣ ጌታችንን ያድነው ዘንድ የተማጸነ፣ ጌታችንም በጥያቄው መሠረት ከመስጠም ያዳነው እንደሆነ ቅዱስ ወንጌል ያስተምረናል፡፡ (ማቴ. ፲፬፥፳፪-፴፫)

በቅፍርናሆም ጉባኤ ጌታን ምሥጢረ ቁርባንን ሲያስተምር አይሁድ ስላልገባቸው ወደ ኋላ አፈገፈጉ። “እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላችሁ?” ብሎ ጌታችን ሐዋርያትን ጠየቃቸው። “ጌታ ሆይ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም የሕይወት ቃል አለህ። እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ እናምናለን” በማለት ሐዋርያትን ወክሎ የመለሰ እርሱ ነው። (ዮሐ. ፮፥፷፮-፷፰)

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እረኛው መሞትና ስለ በጎቹ መበተን ሲያስተምር ለደቀ መዛሙርቱ “በዚህች ሌሊት ሁላችሁም ትክኛላችሁ” ብሎ በተናገረ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ “ሁሉም ቢክዱህ እንኳ እኔ ከቶ አልክድህም” (ማቴ. ፳፮፥፴፬) ብሎ ተናግሯል፡፡ ነገር ግን በዚያው ሌሊት ጌታችን በአይሁድ በምቀኝነት ይሰቅሉት ዘንድ በተያዘ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አስቀድሞ የተናገረውን ቃል ዘንግቶ ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ ክዶታል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ የሚታወቅበት ሌላው ትልቁ ነገር ንስሓው ነው። አምላኩን መበደሉን ሲረዳ ተጸጽቶ ምርር ብሎ የንስሓ ዕንባን አንብቷል፡፡ 

በበዓለ ሃምሳ ለደቀ መዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ ለተሰበሰቡት አይሁድ ወንጌልን የሰበከ፣ ሦስት ሺህ ምእመናንን አሳምኖ የመጀመሪያዋን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የመሠረተ እርሱ ነው። (የሐዋ. ፩፥፲፮-፳፫ ፤ ፪፥፲፬-፴) ልዑል እግዚአብሔር ባደለው ጸጋ ጥላው እንኳን ድውያንን ይፈውስ ነበር። (ሐዋ.  ፭፥፲፭)።

ቅዱስ ጴጥሮስ  በፍልስጥኤም፣  በሶርያ፣  በጳንጦን፣  በገላትያ፣  በቀጰዶቅያ፣ በቢታንያ እና በሮሜ ሰብኳል። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በሮሜ አንድ ዓመት ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ካስተማረ በኋላ የሮሜ ክርስቲያኖች እየበዙ ከመምጣታቸውም በላይ የክርስትናው ጉዞ እስከ ሮማ ባለሥልጣናት ደረሰ። የኔሮን የቅርብ ባለሥልጣናት የሆኑት የአልቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች ወደ ክርስትናው ገቡ። በዚህን ጊዜ ኔሮን ንጉሠ ሮማ በቅንዓት ተነሣባቸው።

ኔሮን በሮም የነገሠው በ፶፬ ዓ.ም. ነው። በመንግሥቱ መጀመሪያ ደግ ሰው ነበረ። ነገር ግን በነገሠ በዓመቱ የጨካኝነት ዐመሉ ብቅ ማለት ጀመረ እና የአባቱን ልጅ አስገደለ። በ፶፱ ዓ.ም. ደግሞ እናቱን በመርዝ ገደለ። በ፷፫ ዓ.ም. እያስተማረ ያሰደገውን መምህሩን ፣ በ፷፪ ዓ.ም. የልጅነት ሚስቱን አግታሺያን አስገደለ። ከእርስዋ በኋላ ያገባትን ሚስቱንም ፓፒያን ገደላት። በ፷፬ ዓ.ም ከከተማው ወጣ ብሎ በሚገኘው ቤተ መንግሥቱ ተቀምጦ የሮማን ከተማ እሳት ለቀቀባት። የሮም ሕዝብ በደረሰው አደጋ እጅጉን ተቆጣ። ኔሮንም በክርስቲያኖች አመካኘ። በዚህም የተነሣ በሮማ ከተማ ሁለት ዓይነት ወሬ መናፈስ ጀመረ።

የሮማ አማልክት በክርስቲያኖች ሃይማኖት ስለተቆጡ በከተማዋ እሳት አዘነቡባት የሚለው የመጀመሪያው ሲሆን ክርስቲያኖች ሆን ብለው ከተማዋን አቃጥለዋታል የሚለው ደግሞ ሁለተኛው ወሬ ነበር። የከተማው መጋየት ያበሳጨው የሮማ ሕዝብ፣ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ እያወጣ መግደሉን ተያያዘው። ይህን የሰሙት የአግቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች (የሮም ባለሟሎች ነበሩ) “አንተ ትረፍልን” ብለው በከተማዋ ግንብ በገመድ አሥረው በቅርጫት በማውረድ ቅጥረ ሮማን ለቅቆ እንዲወጣ አደረጉት።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በኦፒየም ጎዳና ጉዞውን ቀጠለ። ሮማን ለቀቀ። እያዘገመ በሸመገለ ጉልበቱ ሲጓዝ አንድ ቀይ ጐልማሳ ወደ እርሱ ሲመጣ አየ። እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን መሆኑን ተረዳ። ወዲያው በፊቱ ተደፋና “ጌታዬ ወዴት እየተጓዝክ ነው?” አለና ጠየቀው። “ዳግም በሮም ልሰቀል” አለው። በዚህ ሰዓት ቅዱስ ጴጥሮስ አዘነና እንደገና ወደ ሮም ተመለሰ። የኔሮን ወታደሮች እየፈለጉት ነበር። “እነሆኝ ስቀሉኝ” አለ ቅዱስ ጴጥሮስ። ያን ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስን ይዘው አሠሩት። ከጥቂት ቀናት በኋላም ሮማውያን የመስቀያውን እንጨት አቀረቡለት። ያን ጊዜ “እኔ እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም” በማለት ቁልቁል እንዲሰቅሉት ለመነ። እንደለመነውም ሐምሌ ፭ ቀን ፷፯ ዓ.ም ቁልቁል ሰቅለውት በሰማዕትነት ዐረፈ።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዘሩ ከዕብራዊያን፣ ከብንያም ነገድ ሲሆን የተወለደውም በጠርሴስ ከተማ ነው። ጠርሴስ በንግድዋ የታወቀች የኪልቂያ ዋና ከተማ ናት። በከተማዋ እስከ አምስት መቶ ሺህ የሚገመቱ ከየሀገሩ የተሰባሰቡ ሕዝቦች ነበሩባት። ሮማውያን በሥራቸው ለሚተዳደሩት ሕዝቦች ሮማዊ ዜግነትን ይሰጡ ስለነበር፥ የቅዱስ ጳውሎስ አባት በዜግነት ሮማዊ ነበር። ይህም ለቅዱስ ጳውሎስ ተላልፎለታል።

ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ከታወቀው የገማልያል ትምህርት ቤት ገባ። በዚያም የአይሁድን ሕግና ሥርዓት እየተማረ እስከ ፴ ዓመቱ ቆየ። በ፴ ዓመቱ የአይሁድ ሸንጎ አባል ሆኖ ተቆጠረ።ለኦሪታዊ እምነቱም ቀናተኛ በመሆኑ ክርስቲያኖችን ያሳድድ ነበር። ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ ተከሶ በአይሁድ ሸንጎ ፊት በቀረበ ጊዜ በድንጋይ ተወግሮ በሰማዕትነት ሲያርፍ የወጋሪዎችን ልብስ በመጠበቅ የተባበረ ነው። “ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስን በገደሉትም ጊዜ እኔ እዚያ አብረአቸው ነበርሁ፤ የገዳዮችንም ልብስ እጠብቅ ነበር” እንዲል፡፡ (ሐዋ. ፳፪፥፳)

ቅዱስ ጳውሎስ በደማስቆ ከተማ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን ሲሰማ ወደ ሊቀ ካህናቱ ቀርቦ ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የሚያስችለውን የፈቃድ ደብዳቤ አገኘ። ከዚህም በኋላ ጭፍሮችን አስከትሎ ወደ ደማስቆ አመራ። ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ከተማዋ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ነበር ከሰማይ የወረደው ብርሃን አካባቢውን ያለበሰውና “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚለውን ድምፅ የሰማው። ሐዋርያው ጳውሎስም “ጌታ ሆይ ማን ነህ?” ብሎ ጠየቀ። “አንተ የምታሳድደኝ እኔ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ። የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል” ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናገረው። ያን ጊዜም በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ “ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?” ሲል ጠየቀ። ከዚህ በኋላ ተነሥቶ ወደ ደማስቆ እንዲገባ ተነገረው። ነገር ግን ዓይኖቹ ማየት አልቻሉም፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ ሐናንያ ወደሚባል ሰው ወሰዱት፡፡ ሐናንያም እጁን ጭኖ ጸለየ፡፡ ከዓይኖቹም እንደ ቅርፊት ያለ ነገር ተገፎ ወደቀለት፣ ዓይኖቹም ተገለጡ፣ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ ስለ ጌታችንም “የእግዚአብሔር ልጅ ነው” በማለት መስበኩን ቀጠለ፡፡ (የሐዋ. ፱፥፩-፲፰)

አይሁድም ቅዱስ ጳውሎስን ይገድሉት ተነሡ። ሐዋርያት ግን የቅዱስ ጳውሎስን መመለስ ለማመን ቢቸገሩም በርናባስ ወስዶ የጳውሎስን መመለስ በመተረክ እንዲያምኑት አደረጋቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጠርሴስ ከተማ ለዘጠኝ ዓመታት ቆይቷል። ከኢየሩሳሌም ውጭ የአሕዛብ ከተማ በነበረችው በአንጾኪያ የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፋ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመጀመሪያው ጉዞ ያደረገው ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ጥሪ በአሕዛብ ሀገር ወንጌልን ለመስበክ ከበርናባስ ጋር ወጡ። በዚህ ጉዞአቸው በጠቅላላው ወደ ሁለት ሺህ ኪሎ ሜትር የሚደርስ መንገድ በእግር ተጉዟል። ይህም ጉዞ የተከናወነው በ፵፮ ዓ.ም. አካባቢ ነው። የተሸፈኑትም ሀገሮች ሲሊንውቂያ፣ ቆጵሮስ፣ ስልማን፣ ጳፋ፣ ጰርጌን፣ ገላትያ፣ ጵስድያ፣ ኢቆንዮን፣ ሊቃኦንያ፣ ልስጥራ፣ደርቤን፣ጵንፍልያ፣አታልያና አንጾኪያ ናቸው።

ሁለተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶ ዓ.ም. ገደማ ነው። በመጀመሪያው ጉዞ ማርቆስ አብሮ ተጉዞ ነበር። ነገር ግን ጵንፍልያ ከተማ ሲደርስ እናቱ ስለናፈቀችው መመለስ በመፈለጉ በርናባስ ወደ ኢየሩሳሌም ይዞት መጣ። ስለዚህም በሁለተኛው ጉዞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲላስን ይዞ ወደ ኪልቂያ ሶርያ ሲጓዝ በርናባስ ደግሞ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ ሄደ። በዚህ ጉዞው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ግሪክ ደርሶአል። የተጓዘባቸውና ያስተማረባቸው ከተሞችም፦ ደርብያ፣ ልስጥራ፣ፍርግያ፣ ገላትያ፣ ሚስያ፣ጢሮአዳ፣ ሳሞትራቄ፣ ናፑሊ፣ ፊልጵስዩስ፣ ተሰሎንቄ፣ በርያ፣አቴና፣ ቆሮንቶስ፣ አንክራኦስ፣ አፌሶን፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌምና አንጾኪያ ናቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ያገኘው በዚሁ ጉዞው በልስጥራ ከተማ ነው።

ሦስተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶፬ ዓ.ም. ሲሆን የተሸፈኑትም ሀገሮች የሚከተሉት ነበሩ። ገላትያ፣ ፍርግያ፣ ኤፌሶን፣ መቄዶንያ፣ ፊልጵስዩስ፣ ቆሮንቶስ፣ ጢሮአዳ፣ አሶን፣ ሚልጢኒን፣ አንጠቀከስዩ፣ ትሮጊሊዩም፣ መስጡ፣ ቆስ፣ ሩድ፣ ጳጥራ፣ ጢሮስ፣ ጵቶልማይስ፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም ናቸው።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከልዩ ልዩ ሀገሮች ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ዕርዳታ ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን በመያዝ ሦስተኛውን ጉዞ አጠናቅቆ ኢየሩሳሌም ገባ። ነገር ግን ኢየሩሳሌም የገባበት ጊዜ የፋሲካ በዓል ስለነበር ከልዩ ልዩ ሀገሮች የተሰበሰቡ አይሁድ በከተማዋ ነበሩ። እነዚህ በዝርወት የሚኖሩ አይሁድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በየሀገራቸው በትምህርቱ የተነሣ ሲቃወሙት የነበሩ ናቸው።

መስበኩን በመቀጠሉ ምክንያት በ፶፰ ዓ.ም በሮም ለቁም እሥር ተዳረገ። የሁለቱን ዓመት የቁም እሥር እንደጨረሰ ወደ ኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ። ይህም በ፷ዎቹ ዓ.ም ነው። በፍርድ ቤቱ በተደረገው ምርመራ የሮሜን ሕግ የሚቃወም ምንም ወንጀል ስላልተገኘበት በነፃ ተለቀቀ፤ ከዚህ በኋላ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አራተኛውንና የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያልመዘገበውን ጉዞውን ያደረገው። ይህ ጉዞው በመታሠሩ አዝነው ተክዘው የነበሩ ክርስቲያኖችን ለማጽናናት የጀመራቸውን ሥራዎች ፍጻሜ ለማየት የተደረገ ጉዞ ነው። በዚህም ጉዞው ኢየሩሳሌምን፣ ኤፌሶንን፣ ሎዶቅያን፣ መቄዶንያን፣ ቀርጤስን፣ ጢሮአዳን፣ ድልማጥያን፣ እልዋሪቆን፣ ኒቆጵልዮን፣ ብረንዲስን፣ ጎብኝቷል። በዚህ የመጨረሻ የስብከት ጉዞው ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል።

በመጨረሻ በ፷፬ ዓ.ም. ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ምን እንደምትመስል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት። የሮም ሕዝብ በከተማው መቃጠል በማዘኑና በማመፁ ነገሩን ሁሉ በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ። በዚህም የተነሣ ክርስቲያን የተባለ ሁሉ መሰደድ፣ መሠየፍ፣ መታረድ እጣ ፈንታው ሆነ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኒቆጵልዮን ከተማ ሲያስተምር በ፷፭ ዓ.ም. ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ። ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታሥሮ ከቆየ በኋላ በ፸፬ ዓመት ዕድሜው በሮም ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሰይፎ በ፷፯ ዓ.ም. ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት፣ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ዐስራ አራት መልእክታትን ጽፈዋል። የቅዱሳኑ ሐዋርያት ረድኤትና በረከታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፤ አሜን።

ምንጭ፦ መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ ፭፤ መጽሐፍ ቅዱስ ሐዲስ ኪዳን፣

           ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ ቁጥር ፩፤ በማኅበረ ቅዱሳን

ማኅበረ ቅዱሳን የድጋፍ ማሰባሰቢያ የዕጣ ትኬት ማዘጋጀቱ ተገለጸ

ማኅበረ ቅዱሳን የተቋማዊ ለውጥ ትግበራን ተግባራዊ በማድረግ አገልግሎቱን እያከናወነ የሚገኝ ሲሆን ይህን ተከትሎ በተከለሰው የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት መሠረት በግቢ ጉባኤያት (በዩኒቨርሲቲዎች እና ኮሌጆች) ለሚማሩ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች በሃይማኖት እና በሥነ ምግባር አንጾ ለማውጣት ለሚተገብራቸው የመምህራን ማፍራት፣ የመመማሪያ መጻሕፍት ዝግጅት፣ እንዲሁም የቨርቹዋል ሥልጠና ማእከል ማቋቋሚያ የሚውል የድጋፍ ማሰባበሰቢያ የዕጣ ትኬት አዘጋጅቷል፡፡ የዕጣ ትኬቱንም ከሐምሌ 01 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሥርጭት እና ሽያጭ መጀመሩን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ አበበ በዳዳ ገልጸዋል፡፡

የዕጣ ትኬቱም ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና ቤተሰቦቻቸው፣ ለማኅበሩ አባላት እና ቤተሰቦቻቸው እንዲሁም ለሌሎች ደጋፊ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን የቀረበ ሲሆን የአንድ ትኬት ዕጣ ዋጋ 100 (አንድ መቶ ብር) ብር መሆኑን አቶ አበበ ገልጸዋል፡፡

የዕጣ ትኬቱም ልዩ ልዩ ሽልማቶችን ያካተተ ሆኖ ተዘጋጅቷል፡፡ ከሽልማቶቹ መካከል፡-

  • ለሰባት ቀናት ወደ ቅድስት ሀገር የኢየሩሳሌም ጉዞ (ጉብኝት)፣
  • ለሰባት ቀናት ወደ ግብጽ ገዳማት ጉዞ (ጉብኝት)፣
  • ለአምስት ቀናት ከአንድ ቤተሰብ ጋር (በአውሮፕላን) ከኢትዮጵያ ገዳማት ወደ አንዱ መንፈሳዊ ጉብኝት እና ሌሎችንም ልዩ ልዩ ዕጣዎችን አካትቷል፡፡

ትኬቱን ከግቢ ጉባኤ ተማሪዎች፣ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት እንዲሁም በማኅበሩ የልማት ተቋማት ሱቆች ማግኘት ትችላላችሁ፡፡

ዕጣው የሚወጣበት ቀን ኅዳር 21 ቀን 2018 ዓ.ም ነው፡፡

ዘገባው፡- የማኅበረ ቅዱሳን ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ነው፡፡ 

በደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና የወሰዱ ሠልጣኞች ተመረቁ

በማኅበረ ቅዱሳን የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በሥሩ ለሚገኙና ከተለያዩ ግቢ ጉባኤያት ለተወጣጡ ፸፮ አገልጋዮች የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና በመስጠት አስመረቀ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩትን አባላት አቅም ለመገንባትና የማኅበሩን እንዲሁም የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በሚገባ የተረዱ፤ መንፈሳዊ ሕይወታቸውም የተስተካከለና አርአያ ሆነው ግቢ ጉባኤን ሊመሩ የሚችሉ የአመራር አባላትን ለማፍራት ታስቦ በክረምት ወቅት በተለያዩ ማስተባበሪያዎች ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት በሐዋሳ እና በወላይታ ሶዶ የሥልጠና ማእከላት የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ በሐዋሳ የሥልጠና ማእከል ከሐዋሳ፣ ከባሌ ሮቤ፣ ከሻሸመኔ፣ ከዲላ ማእከላትና ከቡሌ ሆራ ልዩ ወረዳ ማእከል ከሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ውስጥ ለተመለመሉ ፳፮ አገልጋዮች የደረጃ ሁለት የተተኪ አመራርነት ሥልጠና ከሰኔ ፩ እስከ ሰኔ ፯ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም. ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ሥልጠናዎቹም፡-  

  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመሪነት ሚና ትናንት፣ ዛሬ እና ነገ
  • ኦርቶዶክሳዊነት ሕይወቱና ክህሎቱ
  • የአኀት አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ
  • ዓለማዊነት (Secularism) ከኦርቶዶክስ እሳቤና ኑሮ አንጻር
  • ማኅበረ ቅዱሳን ማነው?

በሚሉና ሌሎችም ርእሰ ጉዳዮች ላይ ልምድ ባላቸው መምህራን የተሰጠ ሲሆን ከሥልጠናውና ከአሠልጣኖቹ የሕይወት ተሞክሮና ልምድ ዕውቀት እንዳገኙም ሠልጣኞቹ አስረድተዋል፡፡ በሥልጠናውም ሦስት እኅቶችና ፳፫ ወንዶች ተሳትፈው ሰኔ ፯ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ተጠናቋል፡፡

በተመሳሳይ በወላይታ ሶዶ ማእከል በርእሰ አድባራት ወገዳማት ደብረ መንክራት አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ከአርባ ምንጭ፣ ከወላይታ ሶዶ፣ ከጂንካ፣ ከሆሳዕና እና ከዱራሜ ማእከላት ስር ከሚገኙ ግቢ ጉባኤያት የተመለመሉ ፴፰ ወንዶችና ፲፪ እኅቶች በድምሩ ፶ ሠልጣኞች ከሰኔ ፰ እስከ ፲፬ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም የደረጃ ሁለት አመራርነት ሥልጠና ወስደው ተመርቀዋል፡፡

የደረጃ ሁለት የአመራርነት ሥልጠናው በሐዋሳ ማእከል ከተሰጠው ሥልጠና ጋር ተመሳሳይ ርእሰ ጉዳዮችን ያካተተ ሲሆን በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክትም የተካሄደው ሥልጠና እጅግ ጠቃሚ የሆነና ሊበረታታ የሚገባ መሆኑን ጠቅሰው ሠልጣኞች በተሰጠው ሥልጠና እግዚአብሔርን በመፍራት ሕይወታችሁን እንድትመሩ፣ የተቀበላችሁትንም መክሊት በማትረፍ፣ በሄዳችሁበት ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ሀገራችሁን ማገልገል ይጠበቅባችኋል” በማለት የአደራ መልእክትና አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡

በሁለቱም ማስተባበሪያዎች በሁለት ዙር በተሰጡት ሥልጠናዎች ፷፩ ወንዶችና ፲፭ ሴቶች በድምሩ ፸፮ የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራር ሠልጣኞች ተሳትፈውበታል፡፡ በሥልጠና ቆይታቸውም ሠልጠኞቹ ስለ አገልግሎትና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚገጥሟትን ፈተናዎች ትሻገር ዘንድ የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲያበረክቱ ኀላፊነት እንዲሰማቸው ያደረገና ጥሩ ተሞክሮም ማግኘት እንዲችሉ የረዳቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የተተኪ አመራርና መምህራን ሥልጠና በመካሄድ ላይ እንደሚገኝ ተገለጸ

ማኅበረ ቅዱሳን በስድስት ማስተባበሪያዎችና በዐሥራ አንድ ሥልጠና ማእከላት የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርና መምህራን ሥልጠና በመስጠት ላይ እንደሚገኝ በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የተቋማዊ ልማት አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪ ሓጋዚ አብርሃ ገለጹ፡፡

የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠናው በመሐል ማእከላት፡- በአዲስ አበባ፣ በአዳማ (በአፋን ኦሮሞ) ፤ በደቡብ ማስተባበሪያ፡- በወላታና ሐዋሳ፤ በምሥራቅ ማስተባበሪያ፡- ድሬዳዋ፤ በሰሜን ምሥራቅ ማስተባበሪያ፡- ደሴ፤ በሰሜን ምዕራብ ማስተባበሪያ ባሕር ዳር፣ ጎንደር፣ ደብረ ማርቆስ ለሰባት ቀናት ሲሰጥ ቆይቶ ተጠናቋል፡፡ በምዕራብ ማስተባበሪያ ጅማ እና በመሐል ማእከላት ማስተባበሪያ ደብረ ብርሃን የሚሰጠው ሥልጠና ደግሞ በሐምሌና ነሐሴ ለማካሄድ ዝግጅት እየተደረገ የሚገኝ ሲሆን ሠልጣኞቹ በየማስተባበሪዎቻቸው በሚገኙ ግቢ ጉባኤያት በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፎች ሲያገለግሉ የነበሩ መሆናቸው ታውቋል፡፡

በዚህ ሥልጠናም “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የመሪነት ሚና፣ የምዕራባዊነትና የአረባዊነት መዳረሻ ከኦርቶዶክሳዊ ሉላዊነት አንጻር፣ የኦርቶዶክሳዊነት ሕይወትና ክሂሎት፣ የአኀትና የምሥራቅ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ” በሚሉና በሌሎችም ዋና ዋና ርእሰ ጉዳዮች ሥልጠናው የተሰጠ ሲሆን ምሽት ላይ በሚኖረው መርሐ ግብርም የግቢ ጉባኤያት የእርስ በርስ የልምድ ልውውጥና ተሞክሮ በተሳካ ሁኔታ ማካሄድ መቻሉን አስተባባሪው ገልጸዋል፡፡

የደረጃ ሁለት የአዳዲስ ተተኪ መምህራን ሥልጠናም በምሥራቅ ማስተባበሪያ ድሬዳዋ እና በሰሜን ምዕራብ ማስተባበሪያ ባሕር ዳር ሲሰጥ ቆይቶ የተጠናቀቀ ሲሆን፤ በጎንደርና በደብረ ማርቆስ የሚሰጠው ሥልጠና በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ በሌሎች ሰባት ማእከላት ደግሞ በሐምሌና በነሐሴ ወራት እንደሚሰጥ ይጠበቃል፡፡

የደረጃ ሁለት መምህራን ሥልጠናው ከ፳፭-፴ ቀናት የሚወስድ ሲሆን ዐሥር ርእሰ ጉዳዮችን እንዳካተተ ተገልጿል፡፡ በዚህም መሠረት “የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ሕይወተ ቅዱሳን፣ ክርስትና በሀገራዊ ጉዳዮች፣ የስብከት ዘዴ፣ ሃይማኖትና ሳይንስ፣” እንዲሁም ሌሎች ርእሰ ጉዳዮች ተካተዋል፡፡ በዚህም መሠረት በደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ፫፻፷፮፣ በተተኪ መምህርነት ፻፵ ከተለያዩ ማእከላት የተውጣጡ ሠልጣኞች እንደተካተቱ ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የተቋማዊ ልማት አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪ ሓጋዚ አብርሃ ገልጸዋል፡፡     

አዲስ አበባ ማእከል የግቢ ጉባኤት ተማሪዎችን አስመረቀ

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል በልዩ ልዩ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መደበኛ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩና በበርካታ ሰንበት ትምህርት ቤቶች መንፈሳዊ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ከአንድ ሺህ ሁለት መቶ ሠላሳ በላይ የግቢ ጉባኤት ተማሪዎችን በማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያምና ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽርሐ ተዋሕዶ አዳራሽ ሰኔ ፳፪ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም አስመረቀ።   

በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ የወንጌል ትምህርት፣ በተመራቂዎች ያሬዳዊ ወረብና የበገና ዝማሬ የቀረበ ሲሆን በከፍተኛ ማዕረግ ለተመረቁ ተማሪዎች የምስጋና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል፡፡

ተመራቂዎች በበኩላቸው በግቢ ጉባኤ ሕይወት ውስጥ ማለፋቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከዓለማዊ ፈተናዎች ጠብቃ እንዳቆየቻቸውና ለውጤታማነታቸው ትልቁን ድርሻ እንደነበራት በመመስከር በቀጣይም በተሰማሩበት የሥራ ዘርፍ ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ኃላፊነታቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል፡፡

በማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያምና ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንና በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ በተከናወኑ መርሐ ግብሮች ላይ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የተመራቂ ቤተሰቦች የተገኙ ሲሆን ተመራቂዎች የአደራ መስቀል ተበርክቶላቸዋል።

በማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያምና ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ስድስት መቶ ሃምሳ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ደግሞ አምስት መቶ ሰማንያ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ማስመረቁን የአዲስ አበባ ማእከል ሚዲያ ክፍል ዘግቧል፡፡

ምንጭ፡-  የአዲስ አበባ ማእከል ሚዲያ ክፍል

ማኅበረ ቅዱሳን በየከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚያስተምራቸውን የግቢ ጉባኤት ተማሪዎችን አሰመረቀ

ማኅበረ ቅዱሳን ላለፉት ዓመታት በየከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መደበኛ ትምህርታቸውን ሲከታተሉና በግቢ ጉባኤያት መንፈሳዊ ትምህርት በመማር ላይ ይገኙ የነበሩ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ከሰኔ 2017 ዓ.ም ጀምሮ ከየማእከላቱ በማስመረቅ ላይ ይገኛል፡፡

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ተማሪዎችን በልዩ ልዩ መርሐ ግብራት በማስመረቅ ላይ መሆናቸውን ተከትሎ ማኅበረ ቅዱሳንም ባሉት መዋቅሮቹ መሠረት ከየማእከላቱ መረጃዎች እየደረሱን ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፡- ጅግጂጋ ዩኒቨርሲቲ፣ አዳማ ሳንስና ቴክሎሎጂ ዩኒቨርሲቲ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ፣ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ፣ ወሎ ዩኒቨርሲቲ፣ ወላታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ፣ ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ … ሌሎችም በማስመረቅና ለማስመረቅ ዝግጅት በማድረግ ላይ እንደሚገኙ የደረሱን መረጃዎች ያለመክታሉ፡፡

በ2017 ዓ.ም ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከተመረቁት መካከል በየትምህርት ክፍሎቻቸውና ከየተቋማቱ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የሜዳልያና የዋንጫ ተሸላሚዎች ሆነዋል፡፡

ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን በፎቶ ግራፍ አስደግፈን እናቀርባለን፡፡ ዝርዝር መረጃዎችን በቀጣይ ይዘን እንመጣለን፡፡

ሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው የእመቤታችን ፴፫ በዓላት አንዱ ሰኔ ፳ ቀን በኬልቄዶን አውራጃ በቂሣርያ አገር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ያለ እንጨት፣ ያለ ጭቃና ያለ ውኃ በሦስት ድንጋዮች በተወደደ ልጇ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የታነጸበት ዕለት ነው፡፡  

ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ ጌታችን በዐረገ በስምንተኛው ዓመት ለፊልጵስዩስ ሰዎች የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ካስተማሩ በኋላ በክርስቶስ ስም አሳምነው በርካታ አሕዛብን በማጥመቅ ቤተ ክርስቲያን ይሠራላቸው ዘንድ ፈለጉ፡፡ ነገር ግን ጌታችን በሊቀ ሐዋርያነት የሾመው ቅዱስ ጴጥሮስ እያለ እንዴት እኛ ይህንን እናደርጋለን? በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ ወደ ፊልጵስዩስ ይመጣ ዘንድ መልእክት ላኩበት፡፡ እርሱም ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር መጥቶ ከቅዱስ ጳውሎስ እና ቅዱስ በርናባስ ጋር በኢየሩሳሌም ተገናኙ፡፡

በዚያም በአንድነት ሱባኤ ይዘው ከቆዩ በኋላ ጌታችን የሞቱትን አስነሥቶ፣ ያሉትንም ከያሉበት ቅዱሳን ሐዋርያትን ጠርቶ በፊልጵስዩስ አገር ሰብስቦ “በእናቴ በድንግል ማርያም ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚሠሩትን የአብያተ ክርስቲያናት ሥራ

ላሳያችሁ፤ ሥርዓቱንም ላስተምራችሁ”ብሎ ወደ ምሥራቅ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያም ሥፍራ ተራርቀው የነበሩ ሦስት ደንጊያዎች ነበሩ፡፡ ጌታችንም ሦስቱን የተራራቁ ድንጋዮችን በተአምራት አቀራርቦ አንሥቶ ጎተታቸው፡፡ ድንጋዮቹም እንደ ሰም ተለጠጡ፣ እንደ ግድግዳም ሆኑ፡፡

ቁመቱን በ፳፬፤ ወርዱን በ፲፪ ክንድ ለክቶ ለቅዱሳን ሐዋርያት ሰጣቸው፡፡ የብርሃን ምሰሶ ከሰማይ ወረደ፣ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም አምሳያ አድርጎ አነጻት ሁለንተናዋም ተጠናቀቀ፡፡ ዛሬም በዕለተ ዐርብ በዕፀ መስቀል ላይ ጌታችን የተቆረሰውን ቅዱስ ሥጋ፣ ያፈሰሰውን ቅዱስ ደም ቅዱሳን መላእክት በብርሃን ፅዋ ቀድተው በዓለም ሁሉ ረጭተውታል፡፡ ስለሆነም የጌታችን ደም በነጠበባቸው ቦታዎች ሁሉ ላይ ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያን ይሠራባቸዋል፡፡  

ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራውም ጌታችን በዐረገ በ፲፱ኛው፤ እመቤታችን በዐረገች በ፬ኛው ዓመት ሰኔ ፳ ቀን ሲሆን፣ በ፳፩ኛው ቀን (በማግሥቱ) ኅብስት ሰማያዊ፣ ጽዋዕ ሰማያዊ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወረደ፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችን ጋር በቅዱሳን መላእክት ታጅበው ከሰማየ ሰማያት መጥቶ እመቤታችንን ታቦት፤ እርሱ ሠራዒ ካህን፣ ሐዋርያትን ልዑካን አድርጎ ቀድሶ ካቈረባቸው በኋላ “እምይእዜሰ አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ፤ ከዛሬ ጀምሮ እናንተም እንደዚህ አድርጉ”ብሎ አዟቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡

የሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ቁመት በነገሥታት ዘመን የነበሩ የ፳፬ቱ ነቢያት፣ ወይም የ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ፤ ወርዱ ደግሞ የ፲፪ቱ ሐዋርያት ምሳሌ ነው፡፡ ሦስቱ ድንጋዮች የሥላሴ አምሳል ሲሆኑ፣ ከታች አቀማመጣቸው ሦስት፤ ከላይ ሕንፃቸው አንድ መሆኑ የሥላሴን ሦስትነትና አንድነት ያመለክታል፡፡ ሐዋርያት የሠሩትም ሦስት ክፍል አድርገው ሲሆን፡- የመጀመሪያው የታቦተ አዳም፤ ሁለተኛው የታቦተ ሙሴ፤ ሦስተኛው የታቦተ ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ዳግመኛም የሦስቱ ዓለማት ማለትም የመጀመሪያው የጽርሐ አርያም፣ ሁለተኛው የኢዮር፣ ሦስተኛው የጠፈር ምሳሌ ነው፡፡

በሌላም በኩል የመጀመሪያው የኤረር፣ ሁለተኛው የራማ፣ ሦስተኛው የኢዮር አምሳል ነው፡፡ በኤረር፡- መላእክት፣ መኳንንት፣ ሊቃናት፤ በራማ፡- ሥልጣናት፣ መናብርት፣ አርባብ፤ በኢዮር፡- ኃይላት፣ ኪሩቤል፣ ሱራፌል ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ዘጠኙ ነገደ መላእክት የዘጠኙ መዓርጋተ ቤተ ክርስቲያን (መዓርጋተ ክህነት) አምሳል ሲሆኑ፣ ይኸውም መላእክት – የመዘምራን፤ መኳንንት – የአናጕንስጢሳውያን፤ ሊቃናት – የንፍቀ ዲያቆናት፤ ሥልጣናት – የዲያቆናት፤ መናብርት – የቀሳውስት፤ አርባብ – የቆሞሳት፤ ኃይላት – የኤጲስ ቆጶሳት፤ ሱራፌል – የጳጳሳት፤ ኪሩቤል – የሊቃነ ጳጳሳት አምሳሎች ናቸው፡፡

በዚህችም ዕለት በቂሣርያው በቅዱስ ባስልዮስ ዘመን እንዲህ ሆነ፡- ቅዱስ ባስልዮስ የእመቤታችንን ቤተ ክርስቲያን ከሠራ በኋላ በውስጧ የሚያኖረውን የእመቤታችንን ሥዕል ሊያሠራ መሳያ ሠሌዳ ፈለገ፡፡ ሰዎችም በአንድ ባለጸጋ ቤት ጥሩ ሠሌዳ እንዳለ ነገሩትና ሄዶ ለባለጸጋው ሠሌዳውን እንዲሰጠው ለመነው፡፡ ባለጸጋውም “የልጆቼ ነው አልሰጥም” አለው፡፡ በትዕቢትም ሆኖ በታነጸቸው ቤተ ክርስቲያን ላይ የስድብን ነገር ተናገረ፡፡ ወዲያውም ወድቆ ክፉ አሟሟት ሞተና ልጆቹ ፈርተው ሠሌዳውን አምጥተው ለባስልዮስ ሰጡት፡፡ እርሱም ያንን ሠሌዳ የእመቤታችንን ሥዕል አሳምሮ ይስልበት ዘንድ ለሠዓሊ ወስዶ ሰጠው፡፡

በዚህም ጊዜ እመቤታችን በራእይ ለቅዱስ ባስልዮስ ተገለጠችለትና ከአመፀኛ ሰው የተገኘ ነውና በዚያ ሰው ሠሌዳ ሥዕሏን እንዳያስል ከለከለችው፡፡ የእመቤታችን ሥዕሏ የተሳለበትን ሠሌዳም የት እንደሚገኝ ነገረችውና ባስልዮስ ሄዶ በታላቅ ክብር አምጥቶ በቤተ ክርስቲያኑ አስቀመጠው፡፡ ከሥዕሏም ሥር ድውያንን ሁሉ የሚፈውስ የዘይት ቅባት መፍሰስ ጀመረ፡፡ በዚህም ብዙዎች ድንቅ የሆነ ፈውስን አገኙ፡፡ የከበረች ሥዕሏ ከተቀመጠበት ምሰሶ ሥር ጸበል ፈለቀና ብዙዎች ተፈወሱ፡፡ ይህም የተፈጸመው የእመቤታችን ቤተ ክርስቲያን በከበረችበት ዕለት በሰኔ ፳፩ ቀን ነው፡፡

ምንጭ፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፳ ቀን፡፡
  • መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መ/ር አፈወርቅ ተክሌ፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፫፻፵፱ – ፫፻፶፩፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር