“ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፡፡” (ዮሐ. ፫፥፲፫)

በዳዊት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ድኅነት በራሱ ፈቃድ፣ በአባቱም ፈቃድ፣ በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የነሣውን የሰውን ልጅ ሥጋ ተዋሕዶ(አምላክነቱ ሳይለወጥ ፍጹም ሰው ሆኖ) በምድር ተመላልሷል። በሥጋ ማርያም ተገልጦ በምድር በነበረበት ጊዜ እውነተኛውን መንገድ አስተምሯል፣ መርቷል፤ ድውያነ ሥጋን በተአምራቱ፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርቱ ፈውሷል፤ ዓይነ ሥውራንን አብርቷል፤ ሽባውን ተርትሯል፤ ጎባጣውን አቅንቷል፤ ሥርዓተ ወንጌልን ሠርቷል፤ ከኃጢአት በቀር ፍጹም ሰው ሆኖ ተመላልሷል።

ጌታችን ወደ ምድር የመጣበትና በምድር ላይ ይመላለስ በነበረበት ወቅት የነበሩ መሠረታዊ ዓላማዎች የጠፉትን የአዳምን ልጆች ፈልጎ ወደ እቅፉ ማስገባት፣ በበደል ምክንያት ከእግዚአብሔር ተለይቶ የነበረን የሰውን ማንነት ከእግዚአብሔር(ከራሱ) ጋር ማስታረቅ፣ በበደል ምክንያት ወደ ዓለም የገባውን የዲያብሎስ ማሰሪያ ለዘለዓለሙ ቆርጦ መጣል፣ በሔዋን ምክንያት ተዘግቶ የነበረን የገነት በር መክፈት፣ በሰው ልጆች ሁሉ ተፈርዶ የነበረን ሞት በሞቱ ድል አድርጎ መሻር፣ በሲዖል ተግዘው በጨለማ የነበሩትን በነፍሱ ወደ ሲዖል በመውረድ በርብሮ ማውጣት ዋነኞቹ ነበሩ። እነዚህንም ሁሉ ፍቅር ስቦት በመዋዕለ ሥጋዌው በአምላክነቱ ሥልጣን ሁሉንም ፈጽሟቸዋል።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአምላክነቱ ሞትን ድል አድርጎ በሦስተኛው ቀን ከሙታን መካከል በኵር ሆኖ ከተነሣ በኋላ ለሐዋርያቱና ለሚወዱት ሁሉ እየተገለጠ ትንሣኤውን በገሃድ ሲያስረዳ፣ መጽሐፈ ኪዳንን፣ የመጻሕፍትን ምሥጢር፣ ሕግጋትንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተምራቸው ለ፵ ቀናት በምድር ቆይቷል። ከዚህም በኋላ ደቀ መዛሙርቱን “እስከ ቢታንያም ወደ ውጭ አወጣቸው፤ እጁንም አንሥቶ በላያቸውም ጭኖ ባረካቸው። እየባረካቸውም ራቃቸው፤ ወደ ሰማይም ዐረገ።”(ሉቃ. ፳፬፥፶-፶፩)

ዕርገት “ዐርገ፣ ከፍ ከፍ አለ፣ ከታች ወደ ላይ ወጣ፣ ዐረገ” ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን “ዕርገት፣ መውጣት፣ ከፍ ከፍ ማለት፣ ማረግ” ማለት ነው።(መዝገበ ቃላት ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፯፻፰) ዕርገት ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲነገር ምሥጢሩ ብዙ ነው፤ በተወዳጅ ሐዋርያው ከሰማይ የወረደው ተብሎ የተነገረለት መድኃኔዓለም ማንም ሳያየው ከሰማይ ወርዶ ብዙዎች እያዩት ከትንሣኤው በኋላ በ፵ኛው ቀን ወደ ቀደመ ክብሩ በርቀት ያይደለ በርኅቀት ዐርጓል። ወደ ሰማይ መውጣቱ ማረጉ የታመነ የሆነው ጌታ አስቀድሞ ስለመውረዱ የተነገረለት፣ የታወቀለት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም “…ወደ ሰማይ የወጣው የወረደው እንደሆነ ዕወቅ…” በማለት በሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ የተነገረውን ያጠነክራል።(ዮሐ አፈ. ክፍ ፳፫፥፳፯)

ጌታችን ከሰማይ የወረደው ንጽሐ ባሕርይው በበደል ምክንያት አድፎበት በግድ ከገነት ወደ ምድር የወረደውን አዳምን ከወደቀበት ሊያነሣው ከወጣበት ሊመልሰው ነው፤ ለዚህም የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ ከኃጢአት በቀር ፍጹም ሰው ሆነ፤ ያለመቀላቀል ያለመጠፋት ሥጋና ለመለኮትበመዋሐዳቸው ምክንያት ዐረገ ተብሎ ተነገረለት እንጂ መለኮትስ በሁሉ የሚገኝ በሁሉ የመላ(ምልዑ) ነው። ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “እግዚአብሔር በእልልታ ጌታችንም በመለከት ድምፅ ዐረገ” (መዝ. ፵፮፥፯) በማለት ያረገው መለኮት በሥጋ ተዋሕዶ አንድ ባሕርይ የሆነ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነ ይመሰክራል።

ቅዱስ ሉቃስም በወንጌሉ “እየባረካቸውም ራቃቸው፤ ወደ ሰማይም ዐረገ።” በማለት የገለጠው በኃጢአት ምክንያት ድቀት አጋጥሞት የነበረ ሥጋ በተዋሕዶተ ቃል ማረጉን ሲናገር “ራቃቸው” አለ፤ ራሱ እግዚአብሔር መሆኑን ሲገልጥም እንደ ሌሎቹ መላእክት እንዳሳረገቸው  ሳይሆን ራሱ በሥልጣኑ “ዐረገ” በማለት ያረገው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ የሆነ እንደሆነ ገለጠ፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና የዮሴፍ ልጅ ነው ብለው ለካዱት ለአይሁድም የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር መሆኑን በመመስከር “ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም” ካለው ከሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ጋር ተባበረ።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመጣጡ ወደ ምድር መውረዱ በትሕትና ነበር፤ ሲያርግ ግን በልዕልና ነበርና “ዐርገ በስብሐት፤ በምስጋና ዐረገ” እንላለን። መውረዱን በትሕትና ባደረገባት ገሊላ ዕርገቱንም ከሠላሳ ሦስት ዓመታት በኋላ በዚሁ በገሊላ በልዕልና፣ በስብሐት፣ በዕልልታ አድርጎባታልና።

ስለዚህ እኛም ዕርገቱን መሠረተ ሃይማኖታችን በሆነው ጸሎተ ሃይማኖት ”በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ” ብለን ዘወትር እንጸልያለን፤ እንመሰክራለንም። አሁንም ከሊቁ ከአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ጋር “አሁንም ከኛ ጋር በዓልን እንዲያደርጉ አባቶችን እንጥራቸው። ከሁሉ በፊት አዳምን እንጥራው፤ እነሆ እግዚአብሔር ከገነት በወጣህ ጊዜ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ ያለው ተፈጸመ፤ እግዚአብሔር ሥጋን ከሴት ልጅህ ለበሰ፤ በአባቱም ቀኝ በሰማያት ተቀመጠ፤ ይህን የወደድኸውን አምላክነት ከሴት ልጅህ በተወለደ በመለኮት ሰው መሆን አገኘኸው እንበለው። የሕያዋን እናታቸው ስለሆንሽ ሕይወት የተባልሽ ሔዋን ሆይ በሴትልጅሽ ደስ ትሰኚ ዘንድ ነዪ፤ ሕይወትን አምጥተሻልና፤ በታተመ አፈ ማኅፀኗ የወለደችው እርሱ በረከትን ካገኙደቀ መዛሙርቱ ጋር ቆማ እያየችው ወደ ሰማያዊው አባቱ ዐረገ” (መጽሐፈ ምሥ. ፳፰፥፲፬) እያልን እናክብር እናመስግን! ከበዓለ ዕርገቱ ረድኤት በረከት ያሳትፈን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

ምንጭ፦ መጽሐፍ ቅዱስ፤ መጽሐፈ ምሥጢር፤ ተንከተም (በሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ)

የቅዱስሲኖዶስመግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ፡፡

በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ከጥቅምት 11 እስከ ጥቅምት 20 ቀን 2017 ዓ.ም. ድረስ መደበኛ ስብሰባውን ሲያካሂድ ሰንብቷል፡፡

ምልዓተ ጉባኤው ልዑል እግዚአብሔርን አጋዥና መሪ በማድረግ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት፣ ስለምጣኔ ሀብት እድገት፣ በሀገራችን እየተከሰቱ ስላሉት ውስጣዊና ውጫዊ ፈተናዎች፣ ስለ ሀገር ሰላምና አንድነት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና ሐዋርያዊ ተልእኮ ስለ ሰው ልጅ ሁሉ ደኅንነት በስፋት በመወያየት ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር ጠቃሚ የሆኑ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

በዚሁ መሠረት፡-

  1. ከጥቅምት 4 ቀን እስከ ጥቅምት 9 ቀን 2017 ዓ.ም. ድረስ የተካሄደው ዓለም አቀፍ ጉባኤ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ 43ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ዓለም አቀፍ ስብሰባ ተሳታፊዎች የቀረበው ቃለ ጉባኤና የአቋም መግለጫ በሁሉም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አህጉረ ስብከት የበጀት ዓመቱ የሥራ መመሪያ እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
  • በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች እየተከሰተ ባለው የሰላም እጦት፣ የእርስ በርስ ግጭት ምክንያት የሰው ሕይወት እየተቀጠፈ፣ አካል እየጎደለ፣ ማኅበራዊ ትሥሥር እየተናደ፣ ሰብአዊ ክብር እየተጎዳ፣ መብት እየተጣሰ፣ በዜጎች ላይ ሥጋትና አለመረጋጋት እየበዛ ሀብትና ንብረት እየወደመ ስለሆነ ጉዳዩ አስቸኳይ መፍትሔ የሚያስፈልገው መሆኑ አጠያያቂ አይደለም፡፡ ስለሆነም በጦርነትና በግጭት የመጣ ሰላም፣ የተገነባ ሀገር የለምና በሀገራችን እያጋጠመ ያለውን ችግር ለመፍታት ካለፈው በመማር በጥበብ፣ በማስተዋልና በሰለጠነ አካሄድ በሰላማዊ መንገድ በመወያየት ችግሩ በእርቅ እንዲፈታ ለሁሉም ወገኖቻችን ቅዱስ ሲኖዶስ የሰላም ጥሪውን በአጽንኦት ያቀርባል፡፡

3. በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና በሥሩ ባሉ ገዳማትና አድባራት ውስጥ እየቀረቡ ያሉ መጠነ ሰፊ የአስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱ ለማድረግ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ጀምሮ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት፣ በክፍላተ ከተሞችና ችግር አለባቸው ተብለው በጥናት በሚለዩት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ላይ የማጣራት ሥራ እንዲሠራና ውጤቱ ለውሳኔ እንዲቀርብ በሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፡፡

4. የኦሲኤን ቴሌቪዥን ስርጭት የተቋረጠ በመሆነ በአዲስ መልክ ሁሉንም የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ተናጋሪዎች ማህበረሰብ ባቀፈ መልኩ አገልግሎት እንዲሰጥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአፋን ኦሮሞ ኔትወርክ በሚል ስያሜ በጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል ውል ተፈርሞ በአዲስ መልክ የሳተላይት ግዥ እንዲፈጸም ሆኖ አስተዳደሩን በተመለከተ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን ድርጅት ጋር በአንድ ሊቀ ጳጳስና ቦርድ ራሱን በቻለ ሥራ አስኪያጅ እየተመራ አገልግሎቱ ከነበረው በተሻለ ሁኔታ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

5. የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ለደቀ መዛሙርት የሚሰጠው የምስክር ወረቀት አድቫንስ ዲፕሎማና ዲግሪ እንዲሆን ሥርዓተ ትምህርቱ ለሚሰጠው የትምህርት ማስረጃ በሚመጥን መልኩ ተሟልቶ፣ ሊኖረው የሚገባው የሰው ኃይል በየዘርፉ ተጠናክሮ ወደ ትግበራ እንዲገባ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፣

6. የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በሥነ ሕንጻና በኪነ ጥበብ በዓለም ደረጃ ከፍተኛ አድናቆትና ክብር የሚሰጠው ከመሆኑ በተጨማሪ በመዐርገ ጵጵስና ፕትርክና የሚሾሙ አባቶች ሥርዓተ ሲመት የሚፈጸምበት፣ ጥንታዊና ታሪካዊ ካቴድራል መሆኑን ታሳቢ በማድረግ ለዕድሳት ሥራው የገንዘብ ድጋፍ እንዲደረግለት ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤ በተጨማሪም ምእመናን እስከ አሁን እንደሚያደርጉት ሁሉ ለእድሳት ሥራው አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ

ያሳስባል፡፡

7. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዐቢይ ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥልና በንቃት እንዲሳተፍ ሁሉንም አህጉረ ስብከት ባቀፈ ሁኔታ የአጀንዳ መረጣና ተሳታፊ የመለየት ሥራ እንዲከናወን ሆኖ ዐቢይ ኮሚቴው የሥራ ዕቅዱንና አፈጻጸሙን ለቋሚ ሲኖዶስ እያቀረበ በማስወሰን እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በአጠቃላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በመንፈስ ቅዱስ እየተመራ ላለፉት ተከታታይ ቀናት በመንፈሳዊ፣ በማኀበራዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ተገቢውን ውሳኔ በማስተላለፍ መደበኛ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቅቋል፡፡ መሐሪና ሁሉን ቻይ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን፣ ለሕዝባችን፣ ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ፍቅሩንና አንድነቱን ይስጥልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፲፯ ..

ኢትዮጵያ አዲስ አበባ

ነገረ ቅዱሳን

መ/ር መስፍን ምትኬ

ክፍል ሦስት

፫. ቅዱሳን የሚባሉት ምን የፈጸሙ ናቸው?

ቅዱሳን እንደየገድላቸውና ትሩፋታቸው በተለያየ አከፋፈል ሊከፈሉ ቢችሉም በአጠቃላይ ግን ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን የፈጸሙ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡

ሀ. ያላቸውን ሁሉ ትተው አምላካቸውን የተከተሉ ናቸው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ እንግዲህ ምን እናገኛለን?” አለው፡፡  ጌታችን ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፡- እውነት እላችኋለሁ የተከተላችሁኝ እናንተ  በዳግም ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በተቀመጠ ጊዜ እናንተም በዐሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ፤ በዐሥራ ሁለቱም ነገደ እስራኤል ትፈርዳላችሁ፡፡” (ማቴ. ፲፱፥፳፯-፳፰፤ ማር. ፲፥፳፱-፴፩)

ለ. ሕይወታቸውን በተጋድሎ ያሳለፉ ናቸው

➢ “መከራን የሚታገሥ ሰው ብፁዕ ነው፤ ተፈትኖ እግዚአብሔር ለሚወዱት ተስፋ ያደረገላቸውን የሕይወት አክሊል ይቀበላልና፡፡” መንፈሳዊ ሰው ረቂቅ ጠላት ያለበት ስለሆነ ሁል ጊዜ የተዘጋጀ ሆኖ መኖር አለበት፡፡ ቅዱሳንም ይህን ጦርነት ዐውቀው በፈተና የጸኑና እስከ ሞት ድረስ የታመኑ ናቸው” (ያዕ.  ፩፥፲፪)

“ገና አልጸናችሁምና ደማችሁን ለማፍሰስ እስክትደርሱ ኀጢአትን ተጋደሉአት፤ አሸንፏትም፤ ተስፋችሁን የምታገኙባትን ትምህርትም ውደዱአት” (ዕብ. ፲፪፥፬)

➢ መጋደላቸውም ከውስጣዊ እና ውጫዊ (አፍአዊ) ፈተናዎች ጋር ነው፡፡

  • ውስጣዊ ፈተና፦ ይህ ፈተና አንድ ሰው “ሰው” በመሆኑ የሚፈተነው ፈተና ነው፡፡ ይኸውም ከሰዋዊ ባሕርይ ጋር የተያያዘ በመሆኑ ከዚህ ፈተና የሚሸሹት ሜዳ፣ የሚሸሸጉበት ጓዳ የለም፤ ሰው የነፍሱና ሥጋ ተዋሕዶ ውጤት በመሆኑ በዚህ ዓለም ሕይወት ሲወጣና ሲወርድ ይኖራል፡፡ ሰው በዚህ ዓለም ሕይወቱ ራሱን ለፈጣሪ ለማስገዛት ከራሱ ጋር ብርቱ ተጋድሎ ማድረግ ግድ ይለዋል፡፡

➢ ቅዱስ ጳውሎስ “ሥጋ በመንፈስ ላይ መንፈስ በሥጋ ላይ ይመኛል፡፡ እነዚህም እርስ በእርሳቸው ይቀዋወማሉ፡፡ ስለዚህም የምትወዱትን ልታደርጉ አትችሉም” (ገላ. ፲፥፲፯) ብሎ የገለጸው ይህንን የሰው ሕይወት ያለበትን ብርቱ ጦርነት ለማስገንዘብ ነው፡፡

➢ ስለዚህ “ሰውነቴን እየጎሰምኩ አስገዛዋለሁ” እንዳለ ሐዋርያው ፍቃደ ሥጋችን ለነፍሳችን በጾም በጾሎት በስግደት ልናስገዛ ይገባናል፡፡ (፩ኛ ቆሮ. ፱፥፳፯፤ መዝ. ፷፰፥፲)

  • አፍአዊ (ውጫዊ) ፈተና፡- ሰው የሚፈተነው በውስጣዊ ብቻ ሳይሆን በውጫዊውም ፈተና ጭምር ነው፡፡ ይኸውም በቤተሰብ፣ በጓደኛ፣ በዘመድ፣ በሥራ ቦታ፣ በልማድና ጎጂ ባህል፣ …  ነው፡፡

ሐ. እግዚአብሔርን በራሳቸው (በፍጹም ሰውነታቸው) ያገለገሉ ናቸው፡፡

ጌታችን “እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ” (ማቴ. ፲፮፥፪) በማለት የፍጹምነት መንገድ ተናግሯል፡፡

➢ ሰው በዚህ ዓለም ሲኖር በሕግ ተወስኖ ቤተሰብ መሥርቶ ጌታውን እያገለገለ ይኖራል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔርን በማገልገልና ይህን ዓለም በማሰብ ልቡ ይከፈልበታል፤ ለዚህ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ያገባ ግን ሚስቱን ደስ ሊያሰኝ የዚህን ዓለም ኑሮ ያስባል፡፡” (፩ኛቆሮ. ፯፥፴፫) በማለት የልቡን መከፈል ይገልጻል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ ሲያስተምርም “አንድ ሰው ታላቅ ምሳን አደረገና ብዙ ሰዎችን ጠራ፡፡” ይለናል፡፡ ነገረ ግን በመልእክተኛው የተጠሩት ሁሉ ምክንያት እየፈጠሩ ቀርተዋል፡፡ ወደ ግብዣ ከተጠሩት ውስጥ ሦስተኛው ሰው እንደ ምክንያት ያቀረበው “ሚስት አግብቼአለሁ ስለዚህም ልመጣ አልችልም በለው” አለው መልእክተኛውን። (ሉቃ. ፲፬፥፳)

➢ ስለዚህ ቅዱሳን ምክንያት ሳያደናቅፋቸው ይህን ዓለምን በመናቅ በምናኔ የኖሩ ናቸው፡፡

መ. ሩጫቸውን በድል የተወጡ ናቸው

➢ መንፈሳዊ ተጋድሎ በሩጫ ይመሰላል፡፡ “በእሽቅድምድም ስፍራ የሚሮጡት፥ ሁሉ እንዲሮጡ ነገር ግን አንዱ ብቻ ዋጋውን እንዲቀበል አታውቁምን? እንዲሁም ታገኙ ዘንድ ሩጡ።” (፩ኛ ቆሮ. ፱፥፳፬) በማለት መንፈሳዊውን ሕይወት በሩጫ መስሎ ተናግሯል፡፡

“በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና።” (ያዕ. ፩፥፲፪)

➢ መጋደላችንም ከማን ጋር እንደሆነ ሲገልጽ፦ “መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።” በማለት እንደተናገረው፡፡ (ኤፌ. ፮፥፲፪)

➢ ይህንን ተጋድሎ በትዕግሥት ያጠናቀቁትም፦

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ቅዱሳን ተጋድሎና በኋላም የሚያገኙትን ክብር ሲናገር “መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፥ ሩጫውን ጨርሼአለሁ፥ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፥ ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያስረክባል፥ ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም“ ብሏል፡፡ (፪ኛጢሞ. ፬፥፯-፰)

➢ ብዙ ሯጮች ሩጫውን አብረው እንደሚጀምሩ ሁሉ ከሐዋርያት ጋር ጀምረው ሩጫቸውን ያቋረጡም አሉ፡፡ ለምሳሌ ይሁዳ፤ እንዲሁም ዴማስ ከሉቃስና ጢሞቴዎስ ጋር መንፈሳዊ ሕይወቱን መምራት ጀምሮ ሳያጠናቅቁ አቋርጠዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የተዘጋጀላቸውን አክሊል አጥተዋል።

ሠ. በፍጹም መንፈሳዊ ጥበብ የኖሩ ናቸው

አምላክችንና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እንደ እባብ ልባሞች እንደ ርግብ የዋሆች ሁኑ” በማለት በመንፈሳዊ ጥበብ መኖር እንዲገባ አስታምሯል (ማቴ. ፲፥፮) ምክንያቱም ጠላታችን ረቂቅ አመጣጡም ረቂቅ ነውና ይህንን ረቂቅ ጠላት ለመመከት ጥበብ መንፈሳዊ ያስፈልጋል፡፡

በአጠቃላይ ቅዱሳን፦

ሀ. እስከ ሞት ድረስ የታመኑ ናቸው።

“እስከ ሞት የታመንክ ሁን” (ራእ. ፪፥፲) እንደተባለ እስከ ሕይወታቸው ፍጻሜ ድረስ በጾም በጸሎት ተወስነው በፍጹም ተጋድሎ በአምልኮተ እግዚአብሔር የጸኑ ናቸው።

ለ. በጌታችን በአምላካችንና በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ላይ የተመሠረተችውን ቤተ ክርስቲያን እምነትና ሥርዓት ጠብቀው በማስጠበቅ በአገልግሎት የተጉና የተጋደሉ ናቸው።

ሐ. የእግዚአብሔርን ቃል ንባብ፣ ትርጓሜና ምሥጢር ሳያፋልሱ በማስተማር በሃይማኖት የጸኑ እና ምእመናንንም ያበዙ ናቸው።

መ. በሕይወታቸው ነውር በሃይማኖታቸው ነቀፌታ ያልተገኘባቸው ናቸው።

ሠ. ከዓለም ተለይተው በበረሃ ወድቀው፥ ድንጋይ ተንተርሰው፣ ጤዛ ልሰው፣ ዋሻ ዘግተው፣ ጸብአ አጋንንትን ድምፀ አራዊትን እና ግርማ ሌሊትን ሳይሰቀቁ የኖሩ፤ ስለ ሃይማኖታቸው በመመስከር በሰማዕትነት ያረፉ ናቸው።

ረ. ምትሐት ያይደለ እውነተኛ ተአምራትን በማድረግ የሚታወቁ ናቸው።

ሰ. ከፍጹምነት መዓርግ የደረሱ ናቸው።

“እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተ ፍጹማን ሁኑ” (ማቴ. ፭፥፵፰)

ስለዚህ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፦

➢ ቅዱሳንን እግዚአብሔር እንዳከበራቸው ታከብራቸዋለች

➢ በቅድስና ስም ትጠራቸዋለች፡፡

➢ ከእነርሱ በፊት የቅድስና መዓርግ በተሰጣቸው ሰዎች መዝገብ ስማቸውን በክብር ታኖራለች

➢ ተአምራቸውን ወይም ገድላቸውን ጽፋ በክብር ታስቀምጣለች።

➢ ዐጽማቸው ያለበት ቦታ የሚታወቅ እንደሆነ ሰብስባ በክብር ታስቀምጠዋለች፡፡

➢ በእነርሱ ስም ለጸሎት ለልመናና ለምስጋና የሚሆን መልክእ ትደርሳለች።

➢ ስማቸውንም እየጠራች ትማጸንባቸዋለች፡፡

➢ በእነርሱ ስም ጽላት ትቀርጽላቸዋለች፣ ቤተ ክርስቲያን ታንጽላቸዋለች፡፡

➢ የምእመናንም ስመ ክርስትናቸውን በስማቸው ትሰይማለች።

➢ የሚታሰቡበት ዕለት ትሰጣቸዋለች

➢ የመታሰቢያ ሥዕል ትሥልላቸዋለች፡፡ 

የቅዱሳን መታሰቢያ በቤተ ክርስቲያን

• ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳንን ውለታ አትረሳም፡፡ በአፀደ ሥጋ ያሉትን በማገልገል ያረፉትን ቅዱሳንን ደግሞ በማክበር ገድላቸውን በመጻፍ መታሰቢያቸውን ታደርጋለች፡፡ (ዕብ. ፮፥፲)

“እነርሱ በእምነት ተጋደሉ፤ ነገሥታትን ድል ነሡ፤ ጽድቅን አደረጉ፤ ተስፋቸውን አገኙ፤ የአናብስትን አፍ ዘጉ፡፡ የእሳት ኀይልን አጠፉ፤ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፤ ከድካማቸው በረቱ” (ዕብ. ፲፩፥፴፪)

• ቅዱሳንን ቤተ ክርስቲያን በማነጽ፣ ጽላት በመቅረጽ ታስባቸዋለች፡፡

“በቤቴና በቅጽሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያና ስም እሰጣቸዋልሁ፤ የማይጠፋም የዘለዓለም ስም እሰጣቸዋለሁ፡፡” (ኢሳ. ፶፮፥፭)

• ቤተ ክርስቲያን በቅዱሳን የልደትና የዕረፍት ዕለታት የመታሰቢያ በዓል በማድረግ በቅዳሴና በማኅሌት በማክበር በዓለ ንግሥ ታደርጋለች፡፡ በስማቸው ጠበል ጸዲቅ ታደርጋለች፡፡ (ማቴ. ፮፥፵-፵፪)

• ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳንን የተጋደሉትን ተጋድሎ፣ የደረሰባቸውን ፈተና፣ ከጠላት ዲያብሎስ ጋር ያደረጉትን ጦርነት ድልና አክሊል እስካገኙበት ድረስ ያሉትን ገድላቸውን በመጻፍ ታስባቸዋለች፡፡

“መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ የተጠራህለትንም በብዙም ምስክሮች ፊት በመልካም መታመን የታመንህለትን የዘለዓለምን ሕይወት ያዝ።” (፩ኛጢሞ. ፮፥፲፪)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ነገረ ቅዱሳን

መ/ር መስፍን ምትኬ

ክፍል ሁለት

ቅዱሳንን ማወቃችን ምን ጥቅም አለው?

ሀ. ሰይጣን የብርሃን መልአክ መስሎ እንዳንታለል መከላከያ ይሆኑናል።

ለ. ተኩላዎች በጎችን መስለው እንዳይገቡ እውነተኛ እረኛ ይሆኑናል።

ሐ. ቤተ ክርስቲያን መታሰቢያቸውን ለይታ ለመፈጸምና ለእኛ ለማሳወቅ ያስችላታል።

መ. በክርስቶስ የወይን ግንድነት ላይ ቅርንጫፍ በመሆን ብዙ ፍሬ ያፈሩ የሃይማኖት አባቶቻችንን ዐውቀን ከአታላዮች፣ ከአስመሳዮች፣ ከሐሳውያን እንድንጠበቅ ይረዱናል፡፡

የቅዱሳን ሕይወት

የቅዱሳን ሕይወት የሚነበብ መጽሐፍ ነው፡፡ ይኸውም ለክርስቶስ ወንጌል እንደሚገባ በመኖራቸው (በሕገ ወንጌል በመጽናታቸው) ነው፡፡ (ፊልጵ. ፩፥፳፯) በሕገ ወንጌል ለመጽናት የቻሉትም አስቀድመው ይህን ዓለም በመናቅ ከዓለም በመለየታቸው ነው፡፡

ይህንን በተመለከተ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እኔ ግን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መሰቀል እንጂ በሌላ አልመካም ፤ በእኔ ዘንድ ዓለሙ የሞተ ነው፤ እኔም በዓለሙ ዘንድ የሞትሁ ነኝ” እንዲል፡፡ (ገላ. ፮፥፲፬)

ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስም በበኩሉ “ዓለሙንና በዓለም ያለውን አትውደዱ፤ ዓለሙን የሚወድ ግን የአብ ፍቅር በእርሱ የለም፡፡ በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዐይን አምሮት፣ ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም እንጂ ከአብ አይደለም፡፡ ዓለሙ ያልፋል፤ ምኞቱም ያልፋል፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ሰው ግን ለዘለዓለም ይኖራል” ብሏል (፩ኛዮሐ. ፪፥፲፭-፲፯)  

ቅዱሳን ሃይማኖት በመያዛቸው፣ ምግባር በመሥራታቸው በጾም፣ በጾሎት፣ በስግደት በመወሰናቸው በአጠቃላይ ሰውነታቸውን ቅዱስ መሥዋዕት አድርገው ለእግዚአብሔር በመስጠታቸው ዓለምን አሸንፈዋል፡፡ “ልጆች ሆይ፥ እናንተ ግን ከእግዚአብሔር ናችሁ፤ ክፉውንም አሸንፋችሁታል፤ በዓለም ውስጥ ካለው ይልቅ ከእናንተ ጋር ያለው ይበልጣልና፡፡” (፩ኛዮሐ. ፬፥፬)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “እነርሱ የክርስቶስ አገልጋዮች ቢሆኑም እኔም እንደ ሰነፍ ለራሴ እናገራለሁ፤ እኔ እበልጣለሁ፤ እጅግም ደከምሁ፣ ብዙ ጊዜ ተገረፍሁ፤ ብዙ ጊዜም ታሰርሁ፤ ብዙ ጊዜም ለሞት ተዘጋጀሁ፡፡ አይሁድ አንዲት ስትቀር አምስት ጊዜ ዐርባ ዐርባ ገረፉኝ፡፡ ሦሰት ጊዜ በበትር ደበደቡኝ፣ አንድ ጊዜ በድንጋይ መቱኝ፤ መርከቤ ሦስት ጊዜ ተሰበረች፤ በጥልቁ ባሐር ውስጥ ስዋኝ አድሬ ስዋኝ ዋልሁ፡፡ በመንገድ ዘወትር መከራ እቀበል ነበር፤ በወንዝም መከራ ተቀበልሁ፤ ወንበዴዎችም አሠቃዩኝ፤ … የቀረውን ነገር ሳልቆጥር ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው፡፡” በማለት ስለ ክርስቶስ መከራ መቀበሉን ይገልጻል፡፡ (፪ኛቆሮ. ፲፩፥፳፫-፳፰)

የቅዱሳንን ሕይወት በቅድስና በንጽሕና ያጌጠ በገድልም የተመላ ነው

ንጽሕናቸው፡- ”ከእግዚአብሔር የሚወለድ ሁሉ ኃጢአትን አይሠራም፤ ዘሩ በእርሱ ይኖራልና፤ ኃጢአትንም ለሠራ አይችልም፤ ከእግዚአብሔር ተወልዷልና” እንደተባለው ቅዱሳን  ከኃጢአት የተለዩ ናቸው፡፡ (፩ኛዮሐ. ፫፥፱)

ገድላቸው፡- “የገረፉአቸው፣ የዘበቱባቸውና ያሠሯቸው ወደ ወኅኒ ያገቡአቸውም አሉ፡፡ በመጋዝ የሰነጠቁአቸው፣ በድንጋይ የወገሩአቸው፣ በሰይፍም ስለት የገደሉአቸው አሉ፤ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ለሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በወኅኒ፣ ማቅ፣ ምንጣፍና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ ተጨነቁ፣ ተቸገሩ፣ መከራ ተቀበሉ፣ ተራቡ፣ ተጠሙም፡፡” (ዕብ. ፲፩፥፴፮-፴፰)

➢ኑ ተከተሉኝ ያላቸውን ክርስቶስን መስለውታል፡፡ “እኔ ክርስቶስን እንደምመስለው እኔን ምሰሉ” እንዲል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፲፩፥፩)

➢ ቅዱሳን ክርስቶስን የሚመስሉበትን ሕይወት ያገኙት በጸጋ ነው፡፡ “እነዚህን ደግሞ ጠራቸው የጠራቸውንም እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውን እነዚህን ደግሞ አከበራቸው” በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ገልጾታል፡፡ (ሮሜ ፰፥፳፱-፴)

➢ ‘ቅዱሳን በጸጋ ከብረው ክርስቶስን መሰሉት’ ስንል ሥልጣን ተካከሉት በማለት አይደለም፡፡ ለምሳሌ፡- የሰው ልጅ በእግዚአብሔር መልክ ፈጣሪውን መስሎ በመፈጠሩ እግዚአብሔርን ተካከለው አያሰኝም፡፡ “እግዚአብሔርም አለ፡- ሰውን በአርአያችንና በአምሳላችን እንፍጠር” (ዘፍ. ፩፥፳፮)፡፡

➢ በመሆኑም እግዚአብሔር ቅዱሳንን በጸጋ አክብሮ እንዴት እርሱን እንደመሰሉት ጥቅሶች በማቆራኘት ጥቂቶቹን እንመለከታለን፡-

ሀ. “ኢየሱስ ክርስቶስ የጽድቅ ፀሐይ ነው።” (ሚል. ፬፥፪፣ ማቴ. ፲፯፥፪)

➢ ቅዱሳንን “በአባታቸው መንግሥት እንደ ፀሐይ ያበራሉ” ተብሎላቸዋል፡፡ (ማቴ. ፲፫፥፵፫) ይህን የተናገረላቸው ራሱ ጌታችን ነው፡፡

ለ. “ለሰው ሁሉ የሚያበራ እውነተኛ ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣል” (ዮሐ. ፩፥፲፱)

“በጨለማ የሄደ ሕዝብ ታላቅ ብርሃን አየ፤ በሞት ጥላና በጨለማ ሀገርም ለነበሩ ብርሃን ወጣላቸው።” (ኢሳ. ፱፥፪

“እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” (ዮሐ. ፱፥፭) እንዲል ቅዱሳንንም “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ” ብሏቸዋል፡፡ (ማቴ. ፭፥፲፮)

“የሕይወትን ቃል እያቀረባችሁ እንደ ብርሃን ትታያላችሁ” (ፊል. ፪፥፲፭)

“የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይሆንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም” (ዮሐ. ፰፥፲፪)

ሐ. “ቸር ጠባቂ እኔ ነኝ፤ ቸር ጠባቂ ስለ በጎቹ ነፍሱን ይሰጣል” (ዮሐ. ፲፥፲፩)

➢ ቅዱሳንን ወክሎ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስን “… በጎቼን ጠብቅ፤ … ጠቦቶቼን አሰማራ፤ … ግልገሎቼን ጠብቅ፤ …” (ዮሐ. ፳፩፥፲፭-፲፯)

“በእናንተ ዘንድ ያለውን የእግዚአብሔርን መንጋ ጠብቁ … የእረኞቹ አለቃ በሚገለጥበት ጊዜ የማያልፈውን የክብር አክሊል ትቀበላላችሁ” (፩ኛጴጥ. ፭፥፪-፬)

መ. “እግዚአብሔር ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድርም መካከል መድኃኒትን አደረገ” (መዝ. ፸፫፥፲፪)

➢ ቅዱሳንን “እውነት እላችኋለሁ የተከተላችሁኝ እናንተ በዳግም ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በተቀመጠ ጊዜ እናንተም በዐሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ፤ በዐሥራ ሁለቱም ነገደ እስራኤል ትፈርዳላችሁ፡፡” (ማቴ. ፲፱፥፳፰)

“አስቀድማ በምትመጣው ትንሣኤም ዕድል ያገኘ ብፁዕና ቅዱስ ነው፤ ከእንግዲህ ወዲህ በእነር ላይ ሁለተኛው ሞት ሥልጣን የለውም፥ የእግዚአብሔርና የክርስቶስ ካህናት ይሆናሉና፤ ከእርሱም ጋር ሺህ ዓመት ይነግሣሉ።” (ራእ. ፳፥፮)

“ከእንግዲህም ወዲህ ሌሊት አይሆንም፥ ጌታ አምላክም በእነርሱ ላይ ያበራላቸዋልና የመብራት ብርሃንና የፀሐይ ብርሃን አያስፈልጋቸውም፤ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ይነግሣሉ።” (ራእ. ፳፪፥፭)

ሠ. ቅዱሳን የጸጋ አማልእክት መባላቸው ሊሻር አይችልም።  “በኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዘለዓለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ሁሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራን ከተቀበላችሁ በኋላ ፍጹማን ያደርጋችኋል፤ ያጸናችኋል፤ ልባሞችም ያድርጋችኋል” (፩ኛ ጴጥ. ፭፥፲)

“የኀጢአት ትርፍዋ ሞት ነውና፣ የእግዚአብሔር ጸጋ ግን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የዘለዓለም ሕይወት ነው” (ሮሜ ፮፥፳፫)

“ነገር ግን ለምትበልጠው ጸጋ ቅኑ፤ ደግሞም የምትሻለውን መንገድ አስተምራችኋለሁ፡፡” (፩ኛ ቆሮ. ፲፪፥፴፩)

ይቆየን

ነገረ ቅዱሳን

መ/ር መስፍን ምትኬ

ክፍል አንድ

ቅድስና ምንድን ነው?

ቅዱስ የሚለው ቃል ቀደሰ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም አመሰገነ፣ ለየ፣ መረጠ፣ አከበረ ማለት ነው፤ ስለዚህ ቅዱስ ማለት ልዩ፣ ክቡር፣ ንጹሕ፣ ምስጉን ማለት ነው።

ቅድስና በሁለት ይከፈላል፡፡ እነርሱም፦ የባሕርይና የጸጋ ቅድስና ናቸው፡፡

.  የባሕርይ ቅድስና  

የባሕርይ ቅድስና ለእግዚአብሔር ብቻ ገንዘቡ የሆነ ነው፡፡ ይህም ማለት ቅድስናው ከእርሱ የማይለይ፣ ከማንም ያልተቀበለው፣ ማንም ሊወስድበት የማይችል የራሱ ገንዘብ የሆነ ማለት ነው፡፡

በእርሱ ዘንድ ከቅድስና ሌላ ሊታሰብ የማይችል ርኩሰት የሌለበት ነው፡፡ ስለዚህ “ቅዱስ እግዚአብሔር” ይባላል፡፡ ይህን ቅድስናውንም ሱራፌል ኩሩቤል ያለ ዕረፍት “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸባዖት ፍጹም ምሉዕ ቅድሳተ ስብሐቲከ፤ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች” በማለት የባሕርይ የሆነ ቅድስናውን ያመሰግኑታል፡፡ (ኢሳ. ፮፥፫፤ ራእ. ፬፥፰)

  • ቅድስና ለእግዚአብሔር የባሕርይው ገንዘቡ ስለሆነ ቅድስናን በጊዜ ሂደት ወይም በትሩፋት ያገኘው አይደለም፡፡
  • እግዚአብሔር ሁል ጊዜም ቅዱስ ነው፡፡ ለእግዚአብሔር ቅድስና ተመሳሳይ ወይም ተወዳዳሪ የለውም፡፡ “እንግዲህ እተካከለው ዘንድ በማን መሰላችሁኝ” ይላል ቅዱስ እግዚአብሔር (ኢሳ. ፵፥፳፭)
  • “ለዘለዓለም በአርያም የሚኖር ስሙም ቅዱስ የሆነ፤ በቅዱሳን ላይ አድሮ የሚኖር፣ …” (ኢሳ. ፶፯፥፩፭)
  • “ስሙም ቅዱስ ነው” (ሉቃ. ፩፥፵፭)
  • “ሁሉን የምትገዛ ጌታ አምላክ ሆይ! ሥራህ ታላቅና ድንቅ ነው፤ የአሕዛብ ንጉሥ ሆይ፣ መንገድህ ጽድቅና እውነት ነው፤ ጌታ ሆይ አንተን የማይፈራና ስምህን የማያከብር ነው?  አንተ ብቻ ቅዱስ ነህና” (ራእ. ፭፥፫-፬)

ስለዚህ ለእግዚአብሔር ቅድስና ታላቅ ክብርና ምስጋና ልንሰጥ ይገባናል፡፡ አቻ ተወዳዳሪ የለውም፤ ለሌላውም ልንሰጥ አንችልም፤ የባሕርይ ክብሩ ነውና፡፡

. የጸጋ ቅድስና

ጸጋ ማለት ቸርነት፣ ምሕረት፣ በጎነት፣ ያለ ብድራትና ያለ ዋጋ የሚሰጥ ስጦታ ማለት ነው፡፡ በመሆኑም ከእግዚአብሔር የሚገኝ ማንኛውም ስጦታ ሁሉ ጸጋ ይባላል፡፡ በዚህም መሠረት በባሕርይው ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በረድኤት ያደረባቸው በጸጋ የተዋሐዳቸው የሃይማኖት ሰዎች ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ ይኸውም ሃይማኖት ለመያዝ፣ ምግባር ለመሥራት ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው በማስገዛት ከክሕደት፣ ከጥርጥር፣ ከክፋትና ከርኵሰት በመጠበቃቸው ነው፡፡

እግዚአብሔር ራሱ “እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ” (ዘሌ. ፲፱፥፪) በማለት ሰዎች ቅድስናን ገንዘብ እንዲያደርጉ በቃሉ ያስተማረን፡፡ ይህንንም መሠረት አድርጎ ቅድስ ጴጥሮስ “ነገር ግን የጠራችሁ ቅዱስ እንደሆነ እናንተም እንዲሁ በአካሄዳችሁ ቅዱሳን ሁኑ፡፡ እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ” የሚል ተጽፏልና፡፡ (፩ኛጴጥ. ፩፥፲፫-፲፮)

ቅዱሳን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ በመሆናቸው ቅዱሳን ናቸው፡፡ “እናንተ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆናችሁ የእግዚአብሔር መንፈስም በእናንተ ላይ አድሮ እንደሚኖር አታውቁምን?” (፩ኛቆሮ. ፫፥፲፮-፲፯) ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስም በመልእክቱ “እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ጽድቅን የሚያደርግ ሁሉ ጻድቅ ነው” ብሏል (፩ዮሐ. ፫፥፯)

ከላይ እንደተመለከትነው እግዚአብሔር ቅዱስ ነው ስንል ቅድስና የባሕይው ገንዘቡ መሆኑን ዐውቀን ነው፡፡ ቅዱሳንን ቅዱስ ስንል ደግሞ ቅድስናቸው የጸጋ (የስጦታ) መሆኑን ዐውቀን ነው፡፡ “የጸጋ ስጦታ ልዩ ልዩ ነው፣ እግዚአብሔር ግን አንድ ነው” ተብሎ ተጽፏልና፡፡ ፩ኛቆሮ. ፲፪፥፬)

በቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን ተብለው የሚጠሩት እነማን ናቸው?

፩. ቅዱሳን ሰዎች                                         ፭. ቅዱሳት ዕለታት

፪. ቅዱሳን መላእክት                                  ፮. ቅዱሳት መጻሕፍት

፫. ቅዱሳት ንዋያት                                    ፯.ቅዱሳትመካናት          

፬. ቅዱሳት ሥዕላት

ነገረ ቅዱሳንን መማር (ማወቅ) ለምን አስፈለገ?

፩. ሕይወታቸው የወንጌልን እውነት ይበልጥ ስለሚያስረግጥልን፡-

“ሕዝቡንም ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ በኋላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ።” (ማር. ፰፥፴፬) ይህንንም መሠረት አድርገው ቅዱሳን ሐዋርያት ሁሉን ትተው እንደ አጠራራቸው ሳይጠራጠሩ ተከትለውታል፡፡ “ተከተለኝ” አለው፤ ተነሥቶም ተከተለው።” (ማቴ. ፱፥፱) እንደ ቀራጩ ማቴዎስ ሁሉ ሌሎቹንም ለሐዋርያነት መርጦ የሚሠሩትን ሁሉ ትተው ከተከተሉት በኋላ ያልተመለሰላቸው ጥያቄ ነበራቸው፡፡ ጥያቄውንም ቅዱስ ጴጥሮስ ሐዋርያትን ወክሎ አቅርቧል፡፡ “እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ፤ እንግዲህ ምን እናገኛለን?” ሲል። ጌታችንም መልሶ “እውነት እውነት እላችኋለሁ የተከተላችሁኝ እናንተ በዳግም ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በተቀመጠ ጊዜ እናንተም በዐሥራ ሁለቱ ዙፋን ትቀመጣላችሁ፤ በዐሥራ ሁለቱም ነገደ እስራኤል ትፈርዳለችሁ” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፲፱፥፳፯)

ሐዋርያት ሁሉን ትተው ከተከተሉት በኋላ በአደረበት እያደሩ፣ በዋለበት እየዋሉ የቃሉን ትምህርት፣ የእጁን ተአምራት እያዩ ኖረዋልና በዕለተ ጰራቅሊጦስ መንፈስ ሞልቶባቸው ፍሩሃን የነበሩት ጥቡዓን ሆነዋል፡፡ በሐዋርያት እግር የተተኩት ሐዋርያነ አበውም የሚደርስባቸውን መከራ ሁሉ ታግሠው ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን ተከትለውታል፡፡ የእውነት ምስክርም ሆነዋል፡፡ እንደ ምሳሌም፡-

➢ ዓይኑን ያወጣ ስምዖን ጫማ ሰፊው፣

➢ እጁን የቆረጠ አትናቴዎስ ሊቀ ጳጳሳት ዘአንጾኪያ፣

➢ እግሩን የቆረጠ አባ መርትያኖስ፣ … ሌሎችም፡፡

፪. ነገረ ቅዱሳንን ስንማር ከቅዱሳኑ ታሪክ ባሻገር የቅዱሳንን ሁሉ አስገኚ፣ የቅዱሳን ሁሉ ክብርና አክሊል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ላላወቁ ለማሳወቅ፣ ላወቁትም ለማጽናት፡፡ 

“እኔ የወይን ግንድ ነኝ፤ እናንተም ቅርንጫፎቹም እናንተ ናችሁ፤ በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፣ ብዙ ፍሬ የሚያፈራ እርሱ ነው፤ ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና” (ዮሐ. ፲፭፥፭)

“ያዘጋጃቸውን እነርሱን ጠራ፤ የጠራቸውንም እነርሱን አጸደቀ፤ የአጸደቃቸውንም እነርሱን አከበረ” እንዲል፡፡ (ሮሜ ፰፥፴)

“ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳን፣ ንጹሓንና ያለ ነውር የሌለን በፍቅር ያደርገን ዘንድ ለእርሱ መረጠን፤ በኢየሱስ ክርስቶስም እንደ ውድ ፈቃዱ ለእርሱ ልጆች ልንሆነን አስቀድሞ ወሰነን” (ኤፌ. ፩፥፬)

፫. ቅዱሳን የተቀበሉትን መከራ፣ ያሳዩትን ትዕግሥትና ጽናት፣ የከፈሉትን ሰማዕትነት ለምእመናን ያለውን አርአያነት በቃልና በጽሑፍ ለማስተማርና ማንነታቸውን ለማሳወቅ

በእምነትና በሕይወት ቅዱሳንን እንድንመስላቸው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ሲያስተምር “እኔ ክርስቶስን እንደምመስለው እኔን ምሰሉ” (፩ኛቆሮ. ፲፩፥፩) ብሏል፡፡

“የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ፥ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው” (ዕብ. ፲፫፥፯) ቅዱስ ኤፍሬም በሐሙስ ውዳሴ ማርያም፡- “ሰማዕታት የዚህችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ ደማቸውንም ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ፤ ስለ መንግሥተ ሰማያትም መራራ ሞትን ታገሡ” በማለት ስለ እምነታቸው የከፈሉትን መሥዋዕትነት ያመለክተናል፡፡  

፬. ከእግዚአብሔር ያገኙትን የቃል ኪዳን በረከት በተለያየ መንገድ እኛ ምእመናን ተምረን እንድንጠቀምበት፡፡

“ከእነዚህ ከታናናሾቹ ለአንዱ በደቀ መዝሙሬ ስም ቀዝቃዛ ጽዋ ውኃ ብቻ የሚያጠጣ፥ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋውን አያጣም።” (ማቴ. ፲፥፵፪)

፭. ታሪካቸው የቤተ ክርስቲያን ታሪክ አካል በመሆኑ የነበሩበት ዘመን፣ ያበረከቱት አስተዋጽኦና አጠቃላይ ሁኔታዎች በወቅቱ የነበረውን የቤተ ክርስቲያን ሁኔታ ለማወቅና ለመረዳት።

“በዚያ ወራትም በኢየሩሳሌም ባለችው ቤተ ክርስቲያን ላይ ታላቅ ስደት ሆነ፤ ከሐዋርያትም በቀር ሁሉም በይሁዳና በሰማርያ ባሉ አውራጃዎች ሁሉ ተበተኑ። (ሐዋ. ፰፥፩)

፮. መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ማጥናት ስለሚቆጠር

➢ የሐዋርያት ታሪክ መማር የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ማንበብ ነው።

➢ የአስቴር ታሪክ መማር መጽሐፈ አስቴርን ማንበብ ነው።

➢ የሩትን ታሪክ መማር የሩትን መጽሐፍ እንደ ማንበብ ነው።

➢ የአብርሃምን፣ የይስሐቅን፣ የያዕቆብን ታሪክ መማር የኦሪት ዘፍጥረት መጽሐፍን እንደ ማንበብ ነው።

➢ የሳሙኤልን፣ የዳዊትን፣ የሰሎሞንን፣ የኤልያስን፣ የኤልሳዕን፣ የሕዝቅያስን ታሪክ መማር አራቱን መጽሐፍተ ነገሥት እንደ ማንበብ ነው።

፯. ቅዱሳንን ማውቅ ዐውቆም መቀበል፤ እነርሱንም መምሰል ክርስቶስን መመሰል ስለሆነ።

“እውነት እላችኋለሁ፥ በእኔ ካመኑ ከእነዚህ ከታናናሾች ወንድሞቼ ለአንዱ ያደረጋችሁትን ሁሉ ለእኔ አደረጋችሁት” (ማቴ. ፳፭፥፵)

“እውነት እላችኋለሁ ካልተመለሳችሁ እንደዚህም ሕፃን ካልሆናችሁ ወደ መንግሥተ ሰማያት ከቶ አትገቡም፡፡ እንደዚህም ሕፃን ራሱን ዝቅ ያደረገ በመንግሥተ ሰማያት የሚበልጥ ይህ ነው፡፡ እንደዚህም ያለውን አንድ ሕፃን በስሜ የሚቀበል እኔን ይቀበላል፡፡ በእኔ ከሚያምኑ ከእነዚህ ከታናናሾች አንዱን የሚያሰናክል አህያ የሚፈጭበት ወፍጮ በአንገቱ ታስሮ ወደ ጥልቅ ባሕር ቢሰጥም ይሻለዋል፡፡” (ሉቃ. ፲፰፥፫-፮)

“እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል።” (ማቴ. ፲፥፵)

ይቆየን

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ላይ ቅዱስ ፓትርያርኩ ያስተላለፉት መልእክት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

* ብፁዕ አቡነ አብርሃም

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የባሕር ዳር እና የሰሜን ጎጃም አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

* ብፁዕ አቡነ ሄኖክ

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤

*ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!!

እንደዚሁም በዚህ ቀኖናዊና ዓመታዊ የርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ላይ የተገኛችሁ በሙሉ፤ ጸጋንና ሐዋርያነትን ያጐናጸፈን ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅድስት ትንሣኤውን በሰላም አክብረን ይህንን ዓመታዊውን የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ለማካሄድ ስለ ሰበሰበን ክብርና ምስጋና ለእርሱ ይሁን፤ የጉባኤው አባላት የሆናችሁ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትም እንኳን ለርክበ ካህናት ጉባኤ አደረሳችሁ! እንኳንም በሰላም መጣችሁ!

“ረከብነ ጸጋ ወተሰየምነ ሐዋርያተ ከመ ናስምዖሙ ለኣሕዛብ ወይእመኑ በስሙ፡- ከእምነት የሚነሣ መታዘዝ እንዲገኝ ጸጋንና ሐዋርያነትን ተቀበልን” (ሮሜ. ፩÷፭)፤ ይህ ሐዋርያዊ አስተምህሮ የኛን ተልእኮና ተልእኮው ያስፈለገበትን ምክንያት አጉልቶ ያሳያል፤ የተቀበልነው ስጦታም ምን ያህል ታላቅ እንደ ሆነ ምንባቡ ያስረዳል፤ ሐዋርያው በዚህ መልእክት የቅዱስ ወንጌል አስተምህሮ ዋና ግብ ከእምነት የሚነሣ መታዘዝ እንዲገኝ ማድረግ ነው በማለት ያስተምረናል፤ እውነት ነው ድሮውኑም ቢሆን ለእግዚአብሔር መታዘዝ አቅቶን ነው የወደቅነው፤ ዛሬም የምንነሣው ከእምነት የተነሣ መታዘዝን ገንዘብ ስናደርግ ነው፤ ከሁሉ በፊት እምነት ይቀድማል፤ ከሱ በኋላ ደግሞ ለእምነቱ በሙሉ ልብ መታዘዝ ይከተላል፤ ይህ ሲሆን መዳንና ትንሣኤ ይገኛል፤

ዓለም በእግዚአብሔር እየተደረገላት ያለ ጥሪ ይኸው የመታዘዝ ጥሪ ነው፤

ይህንን መለኮታዊ ጥሪ ለዓለም የማድረስ ኃላፊነትም ለኛ ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የተሰጠ እንደሆነ ሐዋርያው አስገንዝቧል፤ ኃላፊነቱ ሲሰጠን ከነ መሳርያው ነው፤ እሱም ጸጋና ሐዋርያነት ነው፤ እኛም እሱን ተቀብለናል፤ እንግዲያውስ የተቀበልነውን ጸጋና ሐዋርያነት በዓለም ውስጥ ላለው ሕዝበ እግዚአብሔር አገልግሎት ማዋል ከኛ ይጠበቃል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በአሁኑ ጊዜ የሌለበት ክፍለ ዓለም የለም፤ ምክንያቱም የዚህ ሲኖዶስ ወኪሎች ሊቃነ ጳጳሳት በአፍሪካ፣ በአውሮፓ፣ በሰሜን አሜሪካ፣ በላቲን አሜሪካ፣ በካናዳና በመካከለኛው ምሥራቅ፣ በእስያና በአውስትራሊያ ወዘተ የሚገኙ ሕዝበ እግዚአብሔር ምእመናንን በማገልገል ላይ ይገኛሉና ነው፤ ይህ ዕድል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መለኮታዊ ተልዕኮውን በአጽናፈ ዓለም ሁሉ ለማድረስ ምቹ መደላድል ፈጥሮለታል፡፡ ከዚህም በመነሣት በየክፍለ ዓለሙ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃነ ጳጳሳት ከትውልደ ኢትዮጵያውያን ባሻገር የየአካባቢውን ሕዝብ በማስተማርና በማቀፍ የተጣለባችሁን ሐዋርያዊ ተልእኮ በትጋትና በንቃት መወጣት ይኖርባችኋል፡፡

በማእከል ሆኖ እየመራ የሚገኝ ቅዱስ ሲኖዶስም ለዚህ ተልእኮ ምቹ መደላድል የመፍጠር ኃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት ይገባዋል፡፡ በተለይም ትምህርተ ሃይማኖትንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የተማሩና በጥልቀት የተገነዘቡ፣ ብስለትም ያላቸው፤ እንዲሁም በቋንቋና በሥነ ልቡና ዕውቀት የላቀ ሀብተ ጸጋ ያላቸውን በሐዋርያነት እያሠለጠነ በአጽናፈ ዓለም ሁሉ  ሊያሰማራ ይገባል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!

በብሂለ አበው (ፀሐይ ለመስኮቷ ሳታበራ…) እንደሚባለው ለሌላው በብቃት መድረስ እንችል ዘንድ እኛ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሲኖዶሱ መንበር በሚገኝባት ምድረ ኢትዮጵያ ከመቸውም የተሻለ ሥራ በመሥራት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ሕዝቡንም ማገልገል ይገባናል፤ ሁላችንም እንደ የምንገነዘበው በሲኖዶሳችን ያልታቀፉ ብዙ ወገኖች በሀገር ውስጥ አሉን፤ እነዚህ ወገኖች አንዳንዶቹ በተለያየ ምክንያት ከኛ የወጡ ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ የሄዱት ወደ ቤታቸው እንዲመለሱ፣ ሌሎችም ወደ መንጋው እንዲቀላቀሉ በርትቶ መሥራት የዚህ ጉባኤ ተቀዳሚ ተልእኮ ነው፤ ምክንያቱም ጸጋንና ሐዋርያነትን የተቀበልንበት ዋናው ምክንያት ይህንን ለማድረግ ነውና፡፡ ከዚህ አኳያ የቤተ ክርስቲያናችን ተደራሽነት በሳሳበት ኣካባቢ ሁሉ የተለየ ትኵረት ሰጥተን መሥራትና ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት ይኖርብናል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውሉደ ክህነትና ምእመናን የሆን ሁላችን፣ ከሁሉ በፊት ያለንን ዓቅምና ብቃት በአግባቡ መገንዘብ ይኖርብናል፤ ለእግዚአብሔር ክብርና ምስጋና ይሁንና ለፈጣሪው በቈራጥነት የሚታዘዝ ምእመን፣ ወጣት፣ ካህን አለን፤ ይህ ትልቅ ጸጋ ነው፤ ይህንን ጸጋ እግዚአብሔር፡- ለእግዚአብሔር መንግሥት በሚመች ሁናቴ ዝቅ ብሎ ማገልገል የክብር ክብር ነው፡፡ በመሆኑም ይህንን የእግዚአብሔር ሕዝብ በሐቅ፣ በቅንነት፣ በትጋትና በታማኝነት ቆመን ካገለገልነውና አባትነታችንንና መሪነታችንን በመልካም አሠራር በትክክል በኅሊናው እንዲቀረጽ ካደረግን፣ ይህ ኃይል ከጐናችን እንደማይለይ እርግጠኞች መሆን እንችላለን፤ ይህንን ካሳካን ለኛ የተሰጠ ኃይልና ብቃት በየትም አይገኝም፡፡

በዚህም በዚያም ሃይማኖቱ የሚጠይቀውን ስብእና እና ቁመና ይዘን ከተገኘን፣ ሕዝበ ክርስቲያኑ ያለውን ብቻ ሳይሆን ሕይወቱን ሳይቀር ለመስጠት ወደ ኋላ የማይል የእግዚአብሔር ሕዝብ አለን፤ ስለዚህ ይህንን ማሳካት እንችል ዘንድ ከእምነት የሚነሣ መታዘዝ እንድናስገኝ የተቀበልነውን ጸጋና ሐዋርያነት በክብር እንያዝ፤

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!!

ለሕዝበ እግዚአብሔር የምናበረክተው አገልግሎት በመንፈሳዊ ብቻ ሳይሆን በኢኮኖሚውና በማኅበራዊው አገልግሎትም ጭምር ነው፤ ከዚህ አንጻር ሕዝባችን የተሻለ ማኅበራዊ አገልግሎት እንዲያገኝ፣ በኢኮኖሚውም ከድህነት የተላቀቀ እንዲሆን፤ እንደዚሁም ሰላሙና አንድነቱ የተጠበቀ እንዲሆን፣ በማስተማርም በተግባር በመሳተፍም የሕዝቡ መሪዎችና አርአያ ሆነን መሥራት ይገባናል፤

በተለይም ከሰላም እጦት የተነሣ በእጅጉ እየተጎዳ ያለውን ሕዝባችን ሰላምና ፍትሕ እንዲያገኝ በጸሎትም በትምህርትም፣ በምክርም ተግተን መሥራት አለብን፤እንዳጋጣሚ ሆኖ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከእንግልት የተላቀቀበት ጊዜ ብዙ እንዳልሆነ ይታወቃል፤ ለእንግልት እየተዳረገ ያለውም የሌሎች እጅ ባይለየውም በዋናነት በገዛ ልጆቹ ነው፤ እናት በገዛ ልጆቿ ስትንገላታ ማየት እጅግ አሳዛኝ ነገር ነው፤ እንደዚህ ያለው ነገር በደንብ ያልታሰበበት አካሄድ በብስለትና በንስሓ ማስተካከል አሸናፊነትን እንጂ ተሸናፊነትን አያሳይምና እንዲታሰብበት እንመክራለን፤ ከዚህ አንጻር ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ልማትና ዕድገት እናሻግራለን ብላችሁ እየደከማችሁ ያላችሁ ወገኖቻችን እባካችሁ መለስ ብላችሁ እናታችሁ የተንገላታችበትን እዩና በቃ በሉ፤ሁሉን የሚያግባባ ነገር ፈልጉና ችግሮችን በሰላማዊ ውይይት ፍቱ፤ በዚህ አማራጭ እናት ሀገር እፎይታ እንድታገኝ አድርጉ፤ ይህንም ለውድ እናት የሚደረግ ካሣ አድርጋችሁ ውሰዱት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ወቅታዊ መልእክትና ጥሪም ይህ ነው፤

በመጨረሻም

የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና አስተዳደራዊ አፈጻጸማችን በመገምገም ለቀጣዩ ጊዜ የሥራ አቅጣጫን የሚያስቀምጠው የርክበ ካህናቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ቀኖናዊ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተጀመረ መሆኑን ለኦርቶዶክሳውያን ሕዝበ ክርስቲያን እናበስራለን፡፡

እግዚአብሔር የተባረከና የተቀደሰ ጉባኤ ያድርግልን!

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

ግንቦት ቀን ፳፻፲፯ .

አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ

“በእንተ ልደታ ለማርያም ፍስሐ ኮነ” (ቅዱስ ያሬድ)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግንቦት ፩ ቀን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከአባቷ ኢያቄምና ከእናቷ ቅድስት ሐና መወለዷን ትመሰክራለች፡፡ (ስንክሳር ግንቦት ፩፣ ተአምረ ማርያም)፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ነቢያት በልዩ ልዩ አገላለጽ በትንቢትና በምሳሌ መስለው ተናግረዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት “በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” (መዝ. ፵፬፥፱) በማለት የተናገረላት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደችባት ዕለት ናት፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስም “ድንግል ትጸንሳለች፤ ወንድ ልጅም ትወልዳለች” (ኢሳ. ፯፥፲፬) ብሎ ትንቢት የተናገረላት ቅድስት ድንግል ማርያም በዚህች ዕለት ተወለደች፡፡ ኢትዮጵያዊው ሊቁ ቅዱስ ያሬድም “ዮም ፍሥሐ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም፤ በማርያም ልደት ምክንያት ዛሬ ደስታ ሆነ!” (ቅዱስ ያሬድ) ብሏል፡፡ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬምም በውዳሴ ማርያም “የመመኪያችን ዘውድ፣ የንጽሕናችንም መሠረት” እያለ ያወደሳት ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደችባት ዕለት ናት፡፡

የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት በራዕይና በምሳሌም አስቀድሞ የተገለጸ ነበር፡፡ ከእነዚህም መካከል ከእርሷ ሰባት ትውልድ አስቀድሞ እንዲሁም ለእናትና ለአባቷ የተገለጹት ምሳሌዎች በቅዱሳት መጻሕፍት በሰፊው ሰፍረው ይገኛሉ፡፡

ታሪኩንም ስንመለከት በቅድስና የሚኖሩ ነገር ግን መካን የነበሩት ቴክታና ጴጥርቃ ነጭ እንቦሳ ከበረታቸው ስትወጣ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ስትደርስ፤ ስድስተኛዪቱ ጨረቃን ጨረቃዋም ፀሐይን ስትወልድ አይተው በሀገራቸው መፈክረ ሕልም (ሕልም ፈች ሊቅ) አለና ሂደው ነገሩት፡፡ ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ፤ ጨረቃይቱ ከፍጡራን በላይ የምትሆን ልጅ ትወልዳላችሁ፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም፤ እንደ ነቢይ እንደ ንጉሥ ያለ ይሆናል አላቸው፡፡ እነርሱም ጊዜ ይተርጉመው ብለውት ሄዱ፡፡ ከዚህ በኋላ ልጅ ወለዱ፡፡ ስሟንም “ረከብኩ ስእለትዬ፤ ረከብኩ ተምኔትዬ›› /የተሳልኩትን አገኘሁ፤ የተመኘሁትን አገኘሁ/ ሲሉ ‹‹ሄኤሜን” አሏት፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና ለአካለ መጠን ስትደርስ ከቤተ ይሁዳ ለተወለደ ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡

ኢያቄምና ሐናም መካን ስለነበሩ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ጸልየው፤ ሲሰጣቸውም መልሰው ለእርሱ እንደሚሰጡ ስዕለትን ተስለው ነበር፡፡ ጸሎታቸው ሲደርስ ለሐና በሕልም ተገልጾላት ለባለቤቷ ለኢያቄም “ብእሴሃ አነኑ ርኢኩ በሕልምየ ርግብ ጸዐዳ መጽአት ኀቤየ ወነበረት ዲበ ርእስየ ወቦአት ውስተ እዝንየ ወኀደረት ውስተ ከርሥየ፤ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብቶ በማሕፀኔ ስትተኛ አየሁ” አለችው፡፡  የዚህ ራእይ ምሥጢርም  ርግብ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትሆን፤ ፀዓዳ (ነጭ) መሆኗ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ዘላለማዊ ድንግልናዋ ነው፡፡ “ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማሕፀኔ ስትተኛ አየሁ” ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በጆሮዋ ሰምታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን የምትፀንሰውን ንጽሕት ርግብ የተባለችውን እመቤታችንን የምትወልድ መሆኗን ሲያጠይቅ ነው፡፡

በተመሳሳይ ኢያቄምም በሕልሙ ያየውን ለባለቤቱ ለሐና “እንዘ ይትረኀዉ ሰብዐቱ ሰማያት ዖፍ ጸዐዳ መጽአ ኀቤየ ወነበረ ዲበ ርእስየ፤ ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ዖፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ” ብሎ በሕልሙ የተገለጸለትን ነግሯታል፡፡ የዚህም ራእይ ምሥጢር ዖፍ የተባለው አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባሕርዩ ነው፡፡ ኢያቄም “ከላይ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ” ማለቱ የኢያቄምን ባሕርይ ባሕርይ እንደሚያደርግ የሚያጠይቅ ሲሆን ሰባቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ልዩ ባህርይው፣ ምልአቱ፣ ስፍሃቱ፣ ርቀቱ፣ ልእልናው፣ መንግሥቱ ናቸው፡፡

በፍጹም ልብ አምኖ ከተራራው ወረደ፤ ለተመሰገነች ሚስቱ ለሐናም ከእግዚአብሔር መልአክ የሰማውን ያንን ራእይ ነገራት። ቃሉ እውነት እንደሆነ እርሷም አመነች። ልዑል እግዚአብሔርንም አመሰገነች። የተመሰገነች ቅድስት ሐናም ከእርሷ የሚወለደውን በዘመኑ ሁሉ ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ታደርገው ዘንድ ለእግዚአብሔር ስዕለትን ተሳለች፡፡

ከዚህም በኋላ ይህችን የከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ፀንሳ ወለደች። ስሟንም ማርያም ብላ ሰየመቻት። ትርጓሜውም እመቤት ነው። ደግሞም ‘ሀብትና ስጦታ ማለት ነው፡፡ በእውነት የዓለሙ ሁሉ እመቤት ሁላችን በእርሷ ሰማያዊ ሀብት ልጅነትን ያገኘንባት ናትና።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዳግም ትንሣኤ

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዐርብ ተሰቅሎ፣ በሦስተኛውም ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል በዝግ መቃብር ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣና በትንሣኤው ትንሣኤአችንን ካወጀልን በኋላ ሐዋርያት በአንድነት ተሰብስበው ሳለ ተገልጦላቸዋል፡፡ ይህንንም ወንጌላውያኑ በመተባበር ገልጸውታል፡፡ በተለይ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ “ያም ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን በመሸ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ አይሁድን ስለ ፈሩ ተሰብስበው የነበሩበት ቤት ደጁ ተቆልፎ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ በመካከላቸው ቆመና ‘ሰላም ለእናንተ ይሁን’ አላቸው፡፡ ይህንም ብሎ እጆቹንና ጎኑን አሳያቸው፤ ደቀ መዛሙርቱም ጌታችንን ባዩት ጊዜ ደስ አላቸው” (ዮሐ. ፳፥፲፱-፳፤ ማቴ. ፳፰፥፲፮-፳፤ ሉቃ. ፳፬፥፴፮-፵፱) በማለት ገልጾታል፡፡

ይህ ሁሉ ሲሆን ግን ዲዲሞስ የተባለው ቶማስ አብሯቸው አልነበረምና የሆነውን ቢነግሩት አላምንም አለ፡፡ ይህንንም ወንጌላውያኑ ሲገልጹት “… ጌታችንን አየነው” አሉት፡፡ እርሱ ግን “የችንካሩን ምልክት በእጁ ካላየሁ፤ ጣቱንም ወደተቸነከረበት ካልጨመርሁ፤ እጄንም ወደ ጎኑ ካላስገባሁ አላምንም” አላቸው፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፬-፳፭)፡፡

ከስምንት ቀን በኋላም ሐዋርያት፣ ካላየሁ አላምን ያለው ቶማስን ጨምሮ በአንድነት ተሰብስበው ባሉበት በሩ እንደተዘጋ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ በመካከላቸውም ቆመ፡፡ እንዲህም አላቸው፡- “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡፡” ከዚህም በኋላ ቶማስን “ጣትህን ወዲህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና ወደ ጎኔ አግባ፤ እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን” አለው፡፡ ቶማስም ”ጌታዬ አምላኬም” ብሎ መለሰ፡፡ ጌታችን ኢየሱስም “ስለአየኸኝ አመንህን? ብፁዓንስ ሳያዩ የሚያምኑ ናቸው” አለው፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፮-፳፱)፡፡

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን ዕለት ዳግም ትንሣኤ ብላ ሰይማ ሥርዓቱንም እንደ ትንሣኤው ትፈጽማለች፣ በድምቀት ታከብራለች፡፡

በዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፡-

  • መልእክታት፡- (፩ቆሮ. ፲፭፥፩-፳)
  •                   :- (፩ዮሐ. ፩፥፩- ፍጻሜው)
  • ግብረ ሐዋርያት፡- (ሐዋ. ፳፫፥፩-፲)
  • ወንጌል፡-       (ዮሐ. ፳፲፱-ፍጻሜው)
  • ቅዳሴ፡-         ዲዮስቆሮስ

ከትንሣኤ ማግሥት እሰከ ዳግም ትንሣኤ የቀናት ስያሜዎች

የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ማግስት አንሥቶ እስከ የሚቀጥለው እሑድ (ዳግም ትንሣኤ) ያሉትን ቀናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለእያንዳንዳቸው ዕለታት ስያሜ ሰጥታ ታስባቸዋለች፡፡ እነዚህንም ቀጥለን እንመለከታቸዋለን፡፡

፩. የትንሣኤ ማግሥት/ ሰኞ ማዕዶት (ሽግግር) ወይም ፀአተ ሲኦል

ነፍሳት ከሲኦል እሥራት ነጻ መውጣታቸው እንዲሁም ከሞት ወደ ሕይወት መሸጋገራቸው የሚታሰብበት ዕለት ነው፡፡ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለ፶፻፭፻ (አምስት ሺህ አምስት መቶ) ዘመን በሲኦል እስራት፣ በጠላት ዲያቢሎስ ግዛት የነበሩትን ነፍሳት ነጻ አውጥቶ አዳምና ልጆቹን ወደ ቀድሞ ርስታቸው የመለሰበት ዕለት መታሰቢያ ነው፡፡ ይህቺን ዕለት አጥተን የነበረውን ነጻነት ማግኘታችንን፣ ባርነቱ ቀርቶ ዳግመኛ ልጆች መሆናችንን፣ ሰላም ይናፍቁ የነበሩ አዳምና ልጆቹ ሰላማቸው ታውጆ፣ ጭንቀታቸው ርቆ፣ በደስታ ወደ ገነት መመለሳቸውን እናስብበታልን፡፡

፪. ማክሰኞ (ቶማስ)

ጌታችን መነሣቱን ለቅዱሳን ሐዋርያተ በገለጸ ጊዜ በቦታው ሐዋርያ ቶማስ አልነበረምና የጌታንን ትንሣኤ ሲነግሩት ካላየሁ አላምንም በማለቱ ጌታችን እርሱ ባለበት ዳግመኛ ለሐዋርያ ተገለጸ፤ ቅዱስ ቶማስንም … ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንክ እንጂ ያላመንክ አትሁን አለው፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፯) ቅዱስ ቶማስም የእጆቹን ጣቶች ጌታችን በዕለተ ዓርብ ሌንጊኖስ በተባለ ጭፍራ በወጋው ጎኑ ሰደደ፤ የዚህን ጊዜ እጁ ኩምትር አለች፤ ቅዱስ ቶማስም ጌታዬ አምላኬ ብሎ መስክሯል፡፡ የዚህን ድንቅ ተአምራት መታሰቢያ ማክሰኞ ይታሰባል፡፡

፫. ረቡዕ (አልዓዛር)

አልአዛር ማለት እግዚአብሔር ረድቷል ማለት ነው፤ ጌታችን ከሞት ያስነሣው የማርያምና የማርታ ወንድም ነው፤ በቢታንያ ይኖር የነበረው የጌታችን ወዳጅ አልዓዛር ታሞ ሞተ፤ በዚህን ጊዜ ጌታችን በዚያ ሥፍራ አልነበረምና እንደ አምላክነቱ ባለበት ቦታ ሆኖ የወዳጁ አልዓዛርን መሞት ዐወቀ፤ ደቀ መዛሙርቱንም ወዳጃችን አልዓዛር ተኝቷል፤ ላነቃው  እሄዳለሁ አላቸው፤ ወደ ቢታንም መጣ ከሞተ ዐራት ቀን የሆነውን አልዓዛርን ከመቃብር አስነሣው፤ ጌታችን ይህን ድንቅ ተአምር ማድረጉን በዚህ ወቅት ታሰባል፡፡ (ዮሐ. ፲፩፥፲፩-፵፬)

፬. ሐሙስ (አዳም ሐሙስ)

አዳም በበደለ ጊዜ በደሉን አምኖ ንስሓ ገባ፤ ተጸጸተ፤ እግዚአብሔርን መበደሉንና ትእዛዙን መጣሱን አምኖ ለብዙ ዓመት ሲያለቅስ ኖረ፤ ጠላትም አስጨንቆ ገዛው፤ የዕዳ ደብዳቤ አጽፎ አዳም ገብሩ ለዲያቢሎስ፣ ሔዋን ዓመቷ ለዲያቢሎስ የሚል የዕዳ ደብዳቤ አጻፋቸው፤ አዳምም ስለ በደሉ መሥዋዕትን ለእግዚአብሔር አቀረበ፤ ጌታችንም የአዳምን መጸጸትና መመለስ ተቀብሎለት አምስት ሺ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጁ ተወልዶ እንደሚያድነው ቃል ኪዳን ገባለት፤ ይህም ዕለት በዚህ ቀን ይታሰባል፤ አዳም ሐሙስ መባሉ ለዚህ ነው፡፡

፭. ዓርብ (ቅድስት ቤተ ክርስቲያን)

በዚህ ዕለት የሚታሰበው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክቡር ደሙ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንደመሠረተ ነው፡፡ በሐዋርያት ሥራ ላይ  ቅዱስ ሉቃስ …እግዚአብሔር በደሙ የዋጃትን ቤተክርስቲያን ትጠብቁ ዘንድ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመ …” በማለት እንደገለጸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ነው፡፡ (የሐ. ፳፥፳፰) ይህ ዕለት የዚህ መታሰቢያው ነው፡፡

፮. ቅዳሜ (ቅዱሳን አንስት)

ከመቶ ሃያው ቤተሰብ መካከል ሰላሣ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት ናቸው፤ የትንሣኤውን ብሥራት ሰምተዋልና … መልአኩም መልሶ ሴቶቹን አላቸው፤ እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ አውቃለሁና፤ እንደተናገረ ተነሥቷልና፤ በዚህ የለም የተኛበትን ሥፍራ ኑና እዩ… በፍርሃትና በታላቅ ደስታም ፈጥነው ከመቃብር ሄዱ፤ ለደቀ መዛሙርቱም ሊያወሩ ሮጡ፤ እነሆም ኢየሱስ አገኛቸውና ደስ ይበላችሁ አላቸው እነርሱም ቀርበው ሰገዱለት፡፡… (ማቴ. ፳፰፥፭-፱) ከትንሣኤ በዓል በኋላ ያለው ቅዳሜ የጌታችንን ትንሣኤ ያበሠሩና የመሰከሩ ቅዱሳን አንስት የሚታሰቡበት ዕለት በመሆኑ ቅዱሳን አንስት ይባላል፡፡

እሑድ (ዳግም ትንሣኤ)

ጌታችን ዐሥሩ ደቀ መዛሙርት ባሉበት ቅዱስ ቶማስ ባልነበረበት ተገልጦ ስለነበር ቅዱስ ቶማስ ባለበት በዚህች ዕለት በዝግ ቤት ሳሉ ተገልጾላቸዋል፤ … ከስምንት ቀን በኋላም ደቀ መዛሙርቱ ደግመው በውስጥ ነበሩ፤ ቶማስም ከእነርሱ ጋር ነበረ፤ ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ ቶማስን ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን” አለው፡፡ ቶማስም “ጌታዬ አምላኬ” ብሎ መለሰለት፡፡”” (ዮሐ. ፳፥፳፮-፳፰) በዚህም የተነሣ ይህ ዕለት ዳግም ትንሣኤ ተብሏል፡፡

መልካም ዘመነ ትንሣኤ!

“ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል” (ዮሐ. ፲፩፥፳፭)

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን……. በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን

አሰሮ ለሰይጣን …….. አግዓዞ ለአዳም

ሰላም.. እምይእዜሰ

ኮነ……. ፍሥሓ ወሰላም

ትንሣኤ የሚለው ቃል “ተንሥአ፤ ተነሣ” ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙ መነሣት ማለት ነው፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ሞቶ ሥጋው ፈርሶና በስብሶ እንደማይቀር እና በዳግም ምጽአት ጊዜ እንደሚነሣ የሚያመለክት ነው፡፡ የሰው ልጅ ከፈጣሪ የተሰጠውን ትእዛዝ ባለመጠበቁ ምክንያት የሞት ሞት ተፈርዶበት ነበረ፡፡ “እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ፣ አትንኩትም” ተብሎ ነበርና፡፡ (ዘፍ. ፫፣፫) በዚህም ምክንያት ከአቤል ጀምሮ እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ የሰው ልጅ በሥጋ የሚሞት ሆኗል፡፡ ነገር ግን እንደሞትን አንቀርም፡፡ ሁላችንም ትንሣኤ አለን፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣት የትንሣኤያችን በኩር ሆኖናልና፡፡(፩ኛ ቆሮ.፲፭፣፳፩)፡፡

“ሞት በሰው በኩል ስለመጣ ትንሳኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኗል” እንዲል፡፡ ፈርሶ በስብሶ መቅረት የቀረልን አካላዊ ቃል ሥጋችን ተዋሕዶ ሰው ሆኖ ሞትን በሞቱ ድል ከነሣልን በኋላ ነው፡፡ ሊቁ በሃይማኖተ አበው “ሞተ ክርስቶስ በሞተ ዚኣነ ከመ ይቅትሎ ለሞት በሞቱ፤ ሞትን በሞቱ ያጠፋልን ዘንድ ክርስቶስ በተዋሐደው ሥጋ የእኛን ሞት ሞተ” ብሎ እንደገለጠው፡፡ (ዮሐ. ፲፩፣፳፭)

“ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ” ያለ ጌታ በጥንተ ትንሣኤ መጋቢት ፳፱ ቀን በዕለተ እሑድ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ መልአኩም (ማር. ፲፮፣፮) “አትደንግጡ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስ ትሻላችሁን? ተነሥቷል” ብሎ ለቅዱሳት አንስት ነግሯቸዋል፡፡ (ሉቃ. ፳፬፣፮)፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ የተነሣው በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ነው፡፡ የትንሣኤያችን በኩር የሆነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱሰስ ክርስቶስ አዳምና ልጆቹን በገባው ቃል ኪዳን መሠረት አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷም ነፍስን ነሥቶ በድንግልና ተፀንሶ በድንግልና ተወለደ፡፡ በዚህ ምድር ላይም እየተመላለሰ ሕይወት የሆነውን ወንጌልን እያስተማረ ድውያንን እየፈወሰ፣ የተራቡትን እያበላ፣ የተጠሙትን እያጠጣ ሠላሳ ሦስት ከሦስት ወራትን በምድር ላይ ቆየ፡፡

ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ በአይሁድ እጅ በፈቃዱ ራሱን ለመከራ መስቀል አሳልፎ ሰጠ፡፡ ከሞተ በኋላም በመቃብር ውስጥ ሦስት ቀንና ሌሊት ቆይቶ ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፤ ቅዱስ ዳዊት፡- “ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትተዋትም” ያለው ይኽንን ታላቅ ምሥጢር በትንቢት ቃል ሲናገር ነው፡፡ (መዝ ፲፭፥፲)፡፡ በትንሣኤውም ለሰው ልጆች ሁሉ ትንሣኤያችንን አበሠረን፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆላሲስዩስ ምእመናን በላከው መልእክቱ “…እርሱም በሁሉ ፊተኛ ይሆን ዘንድ መጀመሪያ ከሙታንም በኩር ነው…” በማለት ገልጾናል፤ (ቆላ. ፩፥፲፰) አባታችን ቅዱስ ኤጲፋንዮስም እንዲህ አስተምሯል፤ “አንድ ሆነው የሚነሡትን ትንሣኤ ዛሬ ተስፋ ያደርጋሉ፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሙታን ትንሣኤያቸው በኩር ነው፤ ከእንግዲህ ወዲህም ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ የተነሣ እርሱ ነው፤ ዳግመኛ ሞት አያገኘውም፡፡ (ሃይ. አበ. ፶፯፥፭)

በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረው የሰው ልጅም ሞቶ በስብሶ የሚቀር ሳይሆን የክብር ትንሣኤን ያገኛል፡፡ ጌታችን መደኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “…ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል…” በማለት በአማናዊ ቃሉ አስተምሮናልና፡፡ (ዮሐ. ፲፩፥፳፭) የሚያምኑበት የሕይወት ትንሣኤ፣ ለማያምኑበትም ደግሞ የዘለዓለም ፍርድ እንደሚጠብቃቸው ሲገልጽ “በመቃብር ያሉ ሁሉ ቃሉን የሚሰሙባት ጊዜ ትመጣለችና ስለዚህ አታድንቁ፡፡ መልካም የሠሩ ለሕይወት ትንሣኤ፣ ክፉ የሠሩም ለፍርድ ትንሣኤ ይነሣሉ” እንዲል (ዮሐ. ፭፥፳፰)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር