“የቀደመውም አለፈ፤ እነሆ ሁሉም አዲስ ሆነ” (፪ቆሮ. ፭፥፲፰)

እንኳን ከዘመነ ማቴዎስ ወደ ዘመነ ማርቆስ በሰላም አሸጋገረን፡፡

መልካም አዲስ ዓመት!

በኢትዮጵያውያን ዘመን አቆጣጠር የመስከረም ወር የወራት ሁሉ መጀመሪያ ነው፡፡ ይህ ወር ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ ገበሬው በክረምቱ ወራት መሬቱን አልስልሶ፣ ዘሩንም ዘርቶ ምድሪቱም አደራዋን ለመመለስ በልምላሜ የምታጌጥበት ወር ነው፡፡ በዚህም ምክንያት እንስሳት ለምለሙን ሣር ግጠው፣ የጠራውን ውኃ ጠጥተው ረክተው፣ አምረው የሚታዩበት የልምላሜ ወር ነው። ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት “ምድርን ጐበኘሃት አጠጣሃትም፥ ብልጥግናዋንም እጅግ አበዛህ፤ የእግዚአብሔርን ወንዝ ውኃን የተመላ ነው፤ ምግባቸውን አዘጋጀህ እንዲሁ ታሰናዳለህና። ትልምዋን ታረካለህ፥ ቦይዋንም ታስተካክላለህ፤ በነጠብጣብ ታለሰልሳታለህ፥ ቡቃያዋንም ትባርካለህ። በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል። የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ፥ ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ። ማሰማርያዎች መንጎችን ለበሱ፥ ሸለቆችም በእህል ተሸፈኑ፤ በደስታ ይጮኻሉ ይዘምራሉም” እንዲል። (መዝ. ፷፬፥፱-፲፫)

ቅዱስ ዮሐንስ

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንም ዓመታትን በቸርነቱ ለሚያቀዳጅ ለእግዚአብሔር ምስጋና ለማቅረብ የአዲሱን ዓመት መጀመሪያ ወይም ርእሰ ዐውደ ዓመት “ቅዱስ ዮሐንስ” በሚል ስያሜ ስታከብረው ኖራለች፣ ትኖራለችም። ይህም ሊሆን የቻለበት ምክንያት የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ ሆኖ መገኘቱና የቤተ ክርስቲያን አበው የበዓላትን ድንጋጌ በወሰኑበት ጊዜ የመጥምቁ ዮሐንስ መታሰቢያ በዓል የኢትዮጵያ ርእሰ ዐውደ ዓመት በሚሆን መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር በየዓመቱ የዘመኑ መጀመሪያ በእርሱ ስም እንዲጠራ በመደንገጋቸው ነው። (ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)፡፡  መጽሐፈ ስንክሳር የዓመቱን መጀመሪያ የሆነውን መስከረምን ሲያትት “ይህ የመስከረም ወር የተባረከ ነው፤ እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው” በማለት ያስረዳል። 

የዘመን መለወጫ

ብርሃናት (ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት) የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ይህ ቀን የዘመን መለወጫ ተብሎ ይጠራል። ሌሊቱ ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ቢቆጥሩ ፫፫፷፬ ቀናት ይሆናል፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ ይህን ሲገልጽ “ሌሊቱም ከቀኑ ጋራ ይተካከላል፡፡ ዓመቱም ጠንቅቆ ቢቆጥሩት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ቀን ይሆናል፡፡ (ሄኖ. ፳፮፥፻፬) ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስም አዲሱን ዓመት በተመለከተ ሲገልጽ “ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድስ” (ሰ.ኤር. ፭፥፳፩) በማለት በኃጢአት የወደቅን በንስሓ ተነሥተን፣ የቀማን መልሰን፣ በአዲስ ሰውነትና በአዲስ አስተሳሰብ ከእግዚአብሔር ጋር እርቅ የምንፈጽምበት፣ በሕይወታችንም እንድንለወጥና እንድታደስ ይመክረናል፡፡

ዕንቁጣጣሽ 

ከሁለት አበይት ምክንያት መጠሪያ እንደሆነ ሊቃውንት ይናገራሉ፤ የመጀመሪያው ምክንያት የኖኅ ልጅ ካም ከወንድሞቹ ጋር ምድርን ሲከፋፈሉ በዕጣ አፍሪካ ስትደርሰው መጀመሪያ ያረፈው ኢትዮጵያ ላይ በመስከረም ወር ሲሆን በዚህ ጊዜ የምድሩንና የአበቦቹን ማማር አይቶ ደስ ብሎት ”ዕንቁ ዕጣ ወጣሽል” ሲል ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል። ሁለተኛው ንጉሡ ሰሎሞን ለንግሥት ሳባ “ዕንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንልሽ” ሲል እጅግ በጣም የከበረ ዕንቁ ያበረከተላት በዚህ በመስከረም ወር ስለነበር፤ ከዚህ በመነሣት መስከረም አንድን እንቁጣጣሽ በሚለው ስያሜ እንደሚጠራ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስተምራሉ።  

ዘመን መለወጫ ከላይ ባየናቸው የተለያየ ስያሜ ይጠራ እንጂ ዘመኑ አዲስ እየተባለ ቢጠራም አዲስ መሆን ያለበት ወርና ወቅቱ ብቻ ሳይሆን የእኛ የክርስቲያኖች ሕይወት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ወንድሞቻችን ሰውነታችሁን ለእግዚአብሔር ሕያውና ቅዱስ፣ ደስ የሚያሰኝም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እማልዳችኋለሁ” እያለ በመዋዕለ ሥጋዌው ያስተምር ነበር፡፡ (ሮሜ ፲፪፥፩)

አዲስ ዓመት ሲመጣ ብዙዎቻችን ያለፈውን አንድ ዓመት፣ ከዚያም በፊት የነበረውን የሕይወት ጉዞአችን መመርመራችን አይቀርም፡፡ እግዚአብሔር ሁልጊዜ አዲስ ቀንን እያፈራረቀ ትናንትን አሳልፎ ዛሬን ይሰጠናል፤ ነገር ግን ከትናንት ስህተታችን ለመማርና እግዚአብሔርን ለመፈለግ የምንሻ፣ ወደ ንስሓም የምንመጣ ስንቶቻችን እንሆን? “አሁንም በክርስቶስ የሆነው ሁሉ አዲስ ፍጥረት ነው፤ የቀደመውም አለፈ፤ እነሆ ሁሉም አዲስ ሆነ” (፪ቆሮ. ፭፥፲፰) እንዲል፡፡ አንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን “በቃ በሚቀጥለው ዓመት ንስሓ እገባለሁ፤ ወይም ዛሬን እንደፈለግሁ ሆኜ ነገ ንስሓ እገባለሁ እያለ በቀቢጸ ተስፋ አይኖርም፡፡

እግዚአብሔር አንድ ቀን አይደለም ዓመት ከዚያም በላይ ታግሶ የሚጠብቀን ልጆቹ ስለሆንን ነው፡፡ ስለዚህ ነገ፣ ነገ እያልን በድንግዝግዝ የምንጓዘውን ጉዞ ትተን ዛሬ ንስሓ መግባት ይገባናል፡፡ በአዲስ ዓመትም ያለፈውን በኃጢአት ጨለማ ውስጥ ተዘፍቀን የኖርንበትን ዘመን ለመድገም ሳይሆን በአዲስ ሰውነት፣ በአዲስ ማንነት እንነሣ ዘንድ ንስሓ እንግባ፣ ከእግዚአብሔር ኅብረት እንጨመር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እላችኋለሁ እንዲሁ ንስሓ ስለሚገባ ስለ አንድ ኃጢአተኛ በእግዚአብሔር መላእክት ፊት በሰማያት ደስታ ይሆናል” በማለት እንዳስተማረን ከተኛንበት እንንቃ፣ በኃጢአት፣ በተንኮል፣ በክፋት የቆሸሸውን ሰውነታችን በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን፣ በመልካም ተግባር አንጽተን ወደ ተቀደሰው አዲስ ሰውነት ልንለወጥ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በዓለ ቅዱስ ሩፋኤል

“ሩፋኤል” የሚለው ቃል “ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ” ማለት ነው፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ጳጉሜን ፫ ቀን በዓሉ በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ “ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ” እንዲል (ጦቢ. ፲፪፥፲፭)፡፡  

በሌላ በኩል ደግሞ ሩፋኤል ማለት ከዕብራይስጥ ሁለት ቃላት ተጣምሮ የተገኘ ቃል ነው፡፡ “ሩፋ” ማለት ጤና፣ ፈውስ፣ መድኃኒት” ማለት ሲሆን “ኤል” የሚለው ቃል ደግሞ በሌሎቹም መላእክት ስም ላይ የሚቀጸል ስመ አምላክ ነው:: ይህ መልአክ እንደ ሌሎቹ ሊቃነ መላእክት ሁሉ ያለ ማቋረጥ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔርን ከሚያመሰግኑ ቅዱሳን መላእክት አንዱ ነው፡፡ የሰው ልጆችንም ይጠብቃቸዋል፣ ያማልዳቸዋል፤ ከፈጣሪም ያስታርቃቸዋል፡፡ (ዘካ.፩÷፲፪፤ ዳን.፬÷፲፫፤ ዘፀ.፳፫÷፳፤ መዝ.፺÷፲፩-፲፫፤ ሉቃ..፲፫፥፮-፱፣)፡፡

የቅዱስ ሩፋኤል በዓሉ የሚከበርባቸው ምክንያቶችም አንደኛው በዓለ ሢመቱን ምክንያት በማድረግ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ቅዳሴ ቤቱ ነው፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቍስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ “በበሽታ ሁሉ ላይ በሰው ልጆችም ቍስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው” በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል (ሄኖ. ፲፥፲፫)፡፡ የሰው ልጆችንም በሥጋ ከታመሙበት ደዌም ሆነ ቍስል ይፈውስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ “በሰው ቍስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው” (ሄኖ. ፮፥፫)፡፡

እግዚአብሔር የመካኒቱን ማኅፀን ፈትቶ የተባረከ ልጅን የመስጠትን ጸጋ ለመላእኩ ቅዱስ ሩፋኤል  ሰጥቶታል፡፡ ሴቶች በሚፀንሱበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያቸውም፡፡ የወላድን ማኅፀን እንዲፈታ ስለተሾመ ከጌታ አዋላጅ ብትኖር ባትኖርም ሐኪም ቅዱስ ሩፋኤል አይታጣም፤ በምጥ ጊዜ ሲጨነቁ ሴቶች ሁሉ የመልአኩን መልክ አንግተው ማርያም ማርያም ብለው ማየ ጸሎቱን ጠጥተው ቶሎ ፈጥነው ይወልዳሉ፡፡ ቅድስት ሣራን እና እንትኩይን (የሳሙኤል እናት) ወልዶ ለመሳም ያደረጋቸው ፈታሔ ማኅፀን የሆነው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሕፃኑ (ኗ በማኅፀን እያለ (ች) ተሥዕሎተ መልክዕ (በሥላሴ አርአያ መልኩ /ኳ/ መሳል) ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ ቅዱስ ሩፋኤል በጥበቃው አይለያቸውም፡፡ በመውለጃቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማኅፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀልላቸዋል፡፡

አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን በወለተ ራጉኤል ላይ አድሮ ባሎቿን እየገደለ ቢያሰቃያት ቅዱስ ሩፋኤል ጋኔኑን አስጨንቆ አስወጥቶላታል (ጦቢ. ፫፥፰-፲፯)፡፡ ለቃየን ልጆች ሰይፍና ሾተል መሥራትን፣ የምንዝር ጌጥ ማጌጥን፣ መቀንደብን ያስተማረ አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አስሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው (ሄኖ. ፪፥፲፰)፡፡ “ዳግመኛም እግዚአብሔር ሩፋኤልን፣ አዛዝኤልን እጁን እግሩን አስረህ በጨለማ ውስጥ ጣለው አለው” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሄኖ. ፫፥፭-፯)፡፡ የጦቢትን ልጁ ጦቢያን በሰው አምሳል ተገልጦ ከተራዳው በኋላ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ራሱን ሲገልጥ “የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነትም ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ አላቸው” (ጦቢ. ፲፪፥፲፭)፡፡

በቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት ከተደረጉ ተአምራት መካከል በእስክንድርያ አቅራቢያ በምትገኝ ደሴት በታነጸች ቤተ ክርስቲያኑ ያደረገው ተአምር አንደኛው ነው፡፡ በመጽሐፈ ስንክሳር እና በድርሳነ ሩፋኤል እንደ ተጻፈው ብዙ ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጠች፤ ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና፡፡ የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ዓሣ አንበሪው ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፡፡ ምእመናኑም ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔር በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ፡፡ ያን ጊዜ ቅዱስ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ “እግዚአብሔር አዝዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጥ ጸጥ ብለህ ቁም!” ባለው ጊዜ አንበሪው ጸጥ ብሎ ቆሟል፡፡ በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገልጠዋል፡፡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆኗል፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል ተረዳኢነት ከሁላችን ጋር ይሁንልን፤ አሜን፡፡

ምንጭ፡- መጽሐፍ ቅዱስ፣ መጽሐፈ ስንክሳር፣ ተአምረ ሩፋኤል

ነገረ ጳጕሜን

በመ/ር ተስፋ ማርያም ክንዴ

በዚህም የመጽሐፍ ቃል መሠረት የኢትዮጵያ ሊቃውንት በዓመት ከ፲፪ቱ ወራት የተረፉትን ዕለታት ከወር ባነሱ ዑደቶች በዕለት፣ በኬክሮስ፣ በካልኢት፣ በሳልሲት፣ በራብኢት፣ በሐምሲትና በሳድሲት ሰፍረውና ቀምረው በዓመት ፭ ቀን፣ ከ፲፭ ኬክሮስ፣ ከ፮ ካልኢት አድርገው እነዚህ ዕለቶች ጳጕሜን ፲፫ኛ ወር አድርገውታል።

ኢትዮጵያዊያንና ግብፃዊያን ብቸኛ የባለ ፲፫ ወር መባላቸው ግን ዕለቷ በሌሎች አልኖር ብላ ሳይሆን ሌሎች እንዲሁ በዘፈቀደ ከሌላው ወር ጋር ደርበው ሲያከብሯት ኢትዮጵያና ግብጽ ግን ከላይ ከኬክሮስ እስከ ሳድሲት ባሉት ጥቃቅን የጊዜ መስፈሪያዎች ሰፍረን ቀምረን ስለምናውላት ነው። የዓለም ሀገራትም አንዳንዶቹ ከወራቸው ደርበው የወሩን ቁጥር አንዳንዴ ፴ አንዳንዴ ፴፩ እያደረጉ አሽባጥን (የካቲትን) ደግሞ ለይተው በ፫ቱ ዓመት ፳፰፣ በ፬ኛው ፳፱ እያደረጉ ጳጉሜን ደርበው ያውሏታል። እንደዚህ ከሚያከብሩ ሀገሮች መካከል ሮማዊያን (አፍርንጅ) እና ሶርያ እንዲሁም ይጠቀሳሉ፤ አንዳንዶቹ ደግሞ በ፰ኛው ወር መጨረሻ ስሟን ለዋህቅ ብለው ስለሚያከብሯት ነው።

በሌላ በኩልም ጳጕሜን ማለት ከህፀፅ ጋር ሲሰላ በዓመት የሚገኝ የፀሐይና የጨረቃ ዑደት ትርፍ ማለት ነው። ማክሰኞ ለረቡዕ አጥቢያ ጨረቃ በምሥራቅ በ፬ኛው ኆኅት በ፬ኛው ኬክሮስ ላይ የ፲፭ ዕለት ሙሉ ጨረቃ ሁና ስትፈጠር ፀሐይ ደግሞ በምዕራብ በኩል ልትገባ ፬ ኬክሮስ (፵፰ ደቂቃ) ሲቀራት ተፈጥራ ወዲያው ገብታለች፡፡  “ወይመይጦ ለብርሃን መንገለ መስዕ፤ ብርሃንን ወደ መስዕ(አቅጣጫ) ይለውጠዋል”  እንዳለ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በሰዓታት መጽሐፉ፡፡ ፀሐይ በሰሜን ዙራ በምሥራቅ ስትወጣ ጨረቃ ለመግባት አንድ ኬክሮስ ፶፪ ካልኢት ፴፩ ሳልሲት ፶፰ ራብዒት ፳፯ ሐምሲት ሲቀራት ደርሳባታለች። ራብዒቱንና ሐምሲቱን ደቃቅ ብሎ ትቶ ሌላውን በትናንሽ የብርሃን መስፈሪያዎች እየተጠቀለለ ሲደመር አንድ ኬክሮስ በዓመት ፮ ዕለት ይሆንና ህፀፅን ሲሰጥ ሌላው ደግሞ ጳጕሜን ያስገኛል።

እንዲሁም ጳጕሜን ማለት ከአንድ ዕለት የተገኘ ትርፍ ብርሃን በዓመት ተጠቅሎ ሲሰላ ማለት ነው። ፀሐይ በአንድ ቀን ወጥታ ፭ቱን ኬክሮስ በአንድ ሰዓት ፷ውን ኬክሮስ በ፲፪ ሰዓት አድርሳ ትገባለች፡፡ በቀን ውስጥ ከዚህ የተረፈ ከመውጣቷ በፊትና ከገባች በኋላ መጠኑ ያነሰም ቢሆን ብርሃን አለ፤ ጳጕሜን ማለት ይህ ብርሃን ነው። ይህም ብርሃን በትናንሽ መስፈሪያዎች ሲለካ ከመውጣቷ በፊት ያለው ፳፮ ካልኢት ፲፭ ነሳልሲት ፴ ራብኢት ከገባች በኋላም እንዲሁ ፳፮ ካልኢት ፲፭ ሳልሲት ፴ ራብኢት ሆኖ በድምሩ በቀን ፀሐይ ከመውጣቷና ከገባች በኋላ ያለው የብርሃን መጠን ፶፪ ካልኢት ከ፴ ሳልሲት ከ፷ ራብኢት ወይም ራብኢቱን ወደ ሳልሲት በመቀየር ፶፪ ካልኢት ከ፴፩ ሳልሲት ይሆናል። ይህንንም በአንድ ላይ እየሰበሰብን ስናሰላው በዓመት ፭ ጳጕሜን ይሰጠናል። ፶፪ቱን ካልኢት እስከ አንድ ወር ስንሰበስበው ወይም ስናባዘው ፲፭፻፷ካልኢ ይሆናል፤ እስከ ዓመት ደግሞ ፲፰ ሺህ ፯፻፳ ካልኢት ይሆናል፤ ይህን ወደ ኬክሮስ ለመቀየር በ፷ ሲገድፉት ወይም ለ፷ ሲያካፍሉት። ፫፻፲፪ ኬክሮስ ይሆናል፤ ይህን ወደ ቀን ለመቀየር በ፷ ሲገድፉት ፭ ቀን ከ፲፪ ኬክሮስ ይሆናል፡፡

ይህን ባለበት እናቆየውና ሌላውን እናስላ ፴ውን ሳልሲት እስከ ወር ሲሰበስቡት ፱፻ ሳልሲት ይሆናል፤ እስከ ዓመት ሲሰበስቡት ደግሞ ፲ሺህ፰፻ ሳልሲት ይሆናል፤ ይህን ወደ ካልኢት ለመቀየር በ፷ ሲገድፉት ፻፹ ካልኢት ይሆናል፤ ወደ ኬክሮስ ሲቀይሩት ፫ ኬክሮስ ይሆናል። ይህን ከመጀመሪያው ጋር ስንደምረው ፭ ዕለት ከ፲፭ ኬክሮስ ይሆናል። እንዲሁም ፷ውን ራብኢት ወደ ካልኢት ሲቀይሩት አንድ ሳልሲት ይሆናል፤ ይህን እስከ ወር ቢወስዱት ፴ ይሆናል፣ እስከ ዓመት ቢወስዱት ደግሞ ፫፻፷ ሳልሲት ይሆንና ወደ ካልኢት ሲቀየር ፮ ካልኢት ይሆናል። ሁሉንም በአንድ ላይ እንሰብስበው፡- ከመጀመሪያው ፭ ቀን ከ፲፭ እና ከመጨረሻው ያገኘነው ፮ ካልኢት በዓመት ፭ ዕለት ከ፲፭ ኬክሮስ ከ፮ ካልኢት ያልነው ይህ ነው።

፲፭ቱ ኬክሮስ በ፬ ዓመት ፷ ኬክሮስ ሆኖ አንድ ዕለት ይሆንና በአራተኛው ዓመት በዘመነ ዮሐንስ ጳጒሜን ፮ ዕለት ትሆናለች። ይህችም ዕለት ሰግረ ዮሐንስ ትባላለች፤ ምክንያቱም የዮሐንስን ዓመት የወር መባቻ እያሰገረች ስለምታውል ነው። ፮ቱ ካልኢት ደግሞ እስከ ፮፻ ዓመት ቢሰበሰብ ፴፮፻ ካልኢት ሆኖ በዕለት አንድ ዕለት ይሆንና በ፮፻ ዓመት ጳጒሜን ሰባት ዕለት ትሆናለች፡፡ ይህችም በቁጥር መምህራን ዘንድ እሪና ዕለት ትባላለች። እሪና መንገዱ ብዙ ነው የቀን እሪና አለ፣ የወር እሪና አለ፣ የዓመት ዕሪና አለ። ዓለም የተፈጠረው በዕሪና ነው የሚያልፈው ግን በእሪና ነው የሚሉ አሉ እሱን ግን ወንጌል ዕለቲቱን የሚያውቅ የለም ስለሚል በዚህ ቀን ምጽአት ይሆናል እያሉ ሰውን ከማደናገር የሰው ዕለተ ምጽአቱ ዕለተ ሞቱ ነውና ሁሌም ተዘጋጅተው እንዲጠብቁ ማስተማር የተሻለ ይሆናል።

ከባንዲራዋ ጋር ነጻነቷንና ሉአላዊነቷን የምታሳይበት መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርጋ በራሷ ሊቃውንት እየቀመረች ለዘመናት ይዛው የመጣችው የራሷ የዘመን ቆጠራ ያላት ኢትዮጵያ በራሷ የዘመን ቆጠራ ሃይማኖታዊ ሥርዓቷን ባህሏንና ማንነቷን ስታከናውን ኑራለች፤ ወደፊትም ትኖራለች። ይህን የማያውቁና የማይረዱ አንዳንድ ግለሰቦችና ድርጅቶች ግን ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ኢትዮጵያ ጳጕሜንን እንደ ሌሎች ሀገሮች ከወሯ ደርባ ማክበር አለባት ወይም መተው አለባት ሲሉ መደመጥ ጀምረዋል።

ለመሆኑ ኢትዮጵያ እነሱ እንዳሉት ጳጕሜን ከሌሎች ወራት ደርባ ብታከብር ምን ነገር ይፋለሳል? ብለው ለሚጠይቁ ሰዎች የሚከተሉትን ጥቂት ማሳየዎች እናቀርባለን።

፩ኛ. ቤተ ክርስቲያናችን በጳጕሜን ወር በርካታ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶችን የምታከናውን ሲሆን ከእነዚህም አንዱ ዕለተ ምጽአትን ታከብራለች። መምህራን ጳጕሜን ከክረምት ወደ በጋው የምንሸጋገርባት ናት፡፡ ክረምት ደግሞ ከላይ ዝናብ ከታች ጎርፍ ነጎድጓድ መብረቅ ወዘተ የሚበዛበት ነውና የዚህ ዓለም ምሳሌ፣ በጋው ደግሞ ክረምቱ የሚያልፍበት ብርሃን የሚወጣበት አዝመራው የሚያፈራበት ነው ብለው ከምጽአት በኋላ በምንወርሰው መንግሥተ ሰማያት ይመስሉና በዚህ ወር ዕለተ ምጽአትን እንድናስብ አድርገውናል። እኛ ክርስቲያኖች ደግሞ ዕለተ ምጽአትን በዚች ወር ብቻ ሳይሆን ዘወትር እሱን እያሰብን ክፉ ከመሥራት እንድንጠበቅ መጽሐፍ ያስተምረናል፡፡ (ማቴ. ፳፬ እና ፳፭) ስለዚህ ጳጉሜን ወር አታክብሩ ማለት ሃይማኖታችሁን፣ ባህላችሁን፣ ታሪካችሁን ተዉ እንደማለት ይቆጠራል፤ ሰው ደግሞ ይህን ማንነት ትቶ እንደ እንሰሳት ሊኖር አግባብ አይደለም።

፪ኛ. በዚህ ወር ከመልአኩ ሩፋኤል በዓል በተጨማሪ በቤተ ክርስቲያን ተሰባስበን ርኅዎ ሰማይን (የሰማይ መከፈት) እናከብራለን። ርኅዎ ሰማይ ጳጕሜን ሦስት ይከበርና ከዚያ ማግስት ያለውን ቀን አንድ ብሎ ቆጥሮ በየ ፶፪ ቀኑ በዓመት ሰባት ጊዜ ይከበራል። ርኅዎ ሰማይ ማለት የሰማይ መከፈት ማለት ነው። በሰማይ መከፈትና መዘጋት ኑሮበት ሳይሆን ጸሎት የሚያርግበት ያልታየ ምሥጢር የሚታይበት እንደሆነ በ(ማቴ. ፫፥፩) ላይ ተጽፎ እናገኘዋለን። ከዚህ በተጨማሪ በጳጕሜን ወር ብዙ ምእመናን በመጾም ጸበል በመጠመቅ ከመንግሥት ሥራ ጀምሮ በነጻ መንፈሳዊና ሥጋዊ ትሩፋቶችን በማከናወን አዲሱን ዓመት ለመቀበል የሚዘጋጁባት ዕለት ናት።

፫ኛ. የጨረቃ ወርኃዊ ልደትና የወቅቶች መፋለስ፡- ጨረቃ የራሷ የቀን፣ የ፲፭ ቀን የወርና የዓመት ዑደት አላት፡፡ ለማሳያ ያህል የያዝነውን ዓመት የ፳፬፲፯ ዓ.ም የዓመት ዑደቷን የምትጨርሰው በፀሐይ ነሐሴ ፲፰ ቀን ነው። ይህ ማለት የመስከረም ጨረቃ ነሐሴ ፲፱ ቀን ትወለዳለች ከነሐሴ ፲፪ ከጳጕሜ ፭ ስናመጣ ፲፯ ይሆናል፡፡ የመስከረም ወር ጨረቃ የምትቆየው ፳፱ ዕለት ስለሆነ ይህን ለመሙላት ከመስከረም ፲፪ እናመጣና በሚቀጥለው ቀን የጥቅምት ጨረቃ ትወለዳለች፤ ስለዚህ ጳጕሜን የለችም ማለት ግን የመስከረም ወር ጨረቃ መስከረም ፲፪ ቀን መጨረሷን ትታ ወደ ፲፯ ትሄዳለች ማለት ነው። ይህ ደግሞ መምህራን ከሠሩት የጨረቃ የወር መንገድና የዓመት መንገድ ጋር የተፋለሰ ይሆናል። አራቱን ወቅቶችንም ብናይ እንደዚሁ መፋለስ ይፈጥራል፡፡ አንድ ቀን ስንል የራሱን ኬንትሮስ ከኬንትሮሱ ጋር የራሱን ፊደል ከፊደሉ ጋር የራሱን የፀሐይ ኆኅት እንዲሁም በመራሒ ወተመራሒ ሕግ የራሱን የቀን የወር የ፲፪ ወርና የዓመት ከዋክብትን ይዞ የሚጓዝ ነው እንጂ እንደፈለገ አንዱን ዕለት ከአንዱ የምንጨምረው አይደለም፡፡ በጥቅሉ በቁጥር መምህራን ዘንድ አንዱን ዕለት እንደፈለግን ከአንደኛው ዕለት ጋር ደርበን እናውል ማለት አንዱን እጅ ከአንዱ እጅ አንዱን እግር ከአንዱ እግር ጋር እንጨምር እንደማለት እንደሚቆጠር ልብ ማለት ይገባል። ሲጠቃለል ኢትዮጵያ የራሷ ባህል ታሪክ ሃይማኖት ያላት ይህንም በትውፊትና በመጽሐፍ ቅዱስ ይዛ የቆየች ሀገር ናት ስለዚህ አንድ ሰው ውሸት ቢናገርና በውሸታሞች መካከል ቢደገፍ ሌሎችም ውሸት ይናገሩ እንደማይባል ኢትዮጵያም ሌሎች በንጉሣቸው በጣኦታቸው ስም በየጊዜው እየቀያየሩ የዘመን ቆጠራን ቢያከብሩ የራሷን እውነት ትታ የእነሱን ውሸት ትቀበል እንደማይባል መረዳት ያስፈልጋል።

ስብሐት ለእግዚአብሔር

በዓለ ደብረ ታቦር!

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐሥሩን ደቀ መዛሙርት በእግረ ደብር ትቶ ሦስቱን የምስጢር ደቀ መዛሙርት የተባሉትን ቅዱስ ጴጥሮስን፣ ቅዱስ ዮሐንስንና ቅዱስ ማርቅዱስን ይዞ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ የወጣበትና በዚያም ከመቃብር ሊቀ ነቢያት ሙሴን፣ ከብሔረ ሕያዋን ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን አምጥቶ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ዕለት በማሰብ ነሐሴ ፲፫ ቀን በየዓመቱ በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

ደብረ ታቦር ከዘጠኙ ዐበይት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓላት አንዱ ሲሆን በዓሉም በምእመናን ዘንድ ቡሄ በመባል ይታወቃል፡፡ በዓለ ደብረ ታቦር ለምን ቡሄ ተባለ? ቡሄ ማለት ‘መላጣ፣ ገላጣ’ ማለት ነው፡፡ ታቦር ተራራ ከገሊላ ባሕር በምዕራባዊ ደቡብ በኵል ዐሥር ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከናዝሬት ከተማ በስተ ምሥራቅ፣ ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተ ምዕራብ አቅጣጫ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል በርካታ ታላላቅ ተራሮች እያሉ ለምን ደብረ ታቦርን መረጠ? ብለን መጠየቃችን አይቀርም፡፡   

ምሥጢረ መንግሥቱን ለምን በታቦር ተራራ ላይ ገለጸ?

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ሌሎች ተራሮች እያሉ ደብረ ታቦር ላይ ክብሩን የገለጠው ስለ ሁለት ምክንያት ነው፡፡ እነርሱም፡- ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ ትንቢቱን ለመፈጸም ማለታችን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፣ ስምህንም ያመሰግናሉ” እያለ እንደዘመረው (መዝ. ፹፰፥፲፪) ይህን ትንቢትንም ለመፈጸም በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ክብረ መንግሥቱን ገለጠ፡፡

ሁለተኛው ደግሞ ምሳሌውን ለመፈጸም ጌታችን በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ተገለጠ፡፡ ቀድሞ ባርቅና ሠራዊቱ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ ወጥተው ሲሳራን ድል አድርገውበታልና (መሳ. ፬፥፮) ጌታም በልበ ሐዋርያት ጥርጥርን እና ፍቅረ ሢመትን (የሥልጣን ፍቅር) ያሳደረ ሰይጣንን ድል ነስቶላቸዋል፡፡ ከዚህም በመነሣት የደብረ ታቦር በዓል “የደቀ መዛሙርት (የተማሪዎች በዓል)” ተብሎም ይጠራል፡፡

እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ሥራ በመሥራታቸው በአሶር በነገሠው በከነዓን ንጉሥ በኢያቡስ እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፤ የሠራዊቱም አለቃ ሲሣራ ነበር፡፡ ዘጠኝ መቶ የብረት ሰረገሎች ነበሩትና የእስራኤልንም ልጆች ሃያ ዓመት አስጨነቃቸው፡፡ (መሳ. ፬፥፩-፫) በዚያም ወራት የለፊዶት ሚስት ነቢይቱ ዲቦራም እስራኤልን ትገዛቸው ነበር፡፡ ባርቅን ጠርታ “ሄደህ ወደ ታቦር ተራራ ውጣ፣ ከአንተም ጋር ከንፍታሌምና ከዛብሎን ልጆች ዐሥር ሽህ ሰዎች ውሰድ፤ እኔም የኢያቢንን ሠራዊት አለቃ ሲሣራን፣ ሰረገሎቹንም፣ ሕዝቡንም ሁሉ ወደ አንተ ወደ ቂሶን ወንዝ እሰበስባለሁ፤ በእጄም አሳልፌ እሰጥሃለሁ” አለችው፡፡ ዲቦራም ከደባርቅ ጋር ወደ ቃዴስ ሄደች፡፡ ሲሣራም ባርቅ ከሠራዊቱ ጋር ወደ ደብረ ተራራ እንደ ወጣ ሰማ፡፡ ባርቅ ሠራዊቱን ይዞ ከደብረ ታቦር ተራራ በወረደ ጊዜ ሲሣራና ሠራዊቱን አስደነገጣቸው፡፡ ሲሣራም ከሰረገላው ወርዶ በእግሩ ሸሸ፡፡ ባርቅም ሲሣራንና ሠራዊትን ድል ነስቶበታል፡፡ (መሳ. ፬፥፩-፲፯)

ሦስቱን ሐዋርያት ብቻ ይዞ ለምን ወደ ደበረ ታቦር ተራራ ወጣ?

፩. ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊሊጶስ ቂሳርያ ደቀ መዛሙርቱን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?” ብሎ ጠየቃቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ!” ብሎ መሰከረ፡፡ (ማቴ. ፲፮፥፲፮) ቅዱስ ጴጥሮስ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት የመሰከረውን ምስክርነት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ይሰሙ ዘንድ፣ ከነቢያት (ሙሴና ኤልያስ) አንደበት ይረዱ፣ በተዓምራት የደነደነ ልባቸውን ይከፍት ዘንድ የጌታችንን ነገረ ተዋሕዶ ከመሰከረ ከስድስት ቀን በኋላ አዕማድ ሐዋርያት ተብለው የተጠሩትን ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ያዕቆብና ቅዱስ ዮሐንስን ይዞ ወደ ተራራ አወጣቸው (ማቴ. ፲፯፥፩-፲)፡፡

፪. ሙሴን ከመቃብር፣ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን ለምን አመጣቸው?

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከሕግ (ከኦሪት)፣ ነቢዩ ኤልያስ ደግሞ ከታላላቅ ነቢያት የተመረጡበት ሌላው ምክንያት እግዚአብሔር በዘመነ ኦሪት ከሙሴ ጋር ቃል በቃል በደመና በሚነጋገርበት ጊዜ ሙሴ “ፊትህን (ክብርህን) አሳየኝ” ብሎ እግዚአብሔርን በጠየቀው ጊዜ “ሰው አይቶኝ አይድንምና ፊቴን ማየት አይቻልህም“ ብሎታል፡፡ በዚህም ብቻ ሳያበቃ “እስከ አልፍም ድረስ እጄን በላይህ እጋርዳለሁ፤ በዚያ ጊዜ ጀርባዬን ታያለህ፤ ፊቴን ግን ለአንተ አታይም” ብሎታል፡፡ (ዘፀ.፴፫፥፲፫-፳፫)

በፊልጶስ ቂሳርያ ጌታ ሐዋርያትን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደሆነ ይሉታል?” ብሎ ለጠየቃቸው ጥያቄ ሲመልሱ “ሙሴ ነው ይሉሃል ፤ እንዲሁም የኃይል ሥራህን ተመልክተው ኤልያስ ነው ይሉሃል” ብለው ነበር፤ ሙሴን ከመቃብር፤ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ “አንተ በኋለኛው ዘመን ምስክር ትሆነኛለህ” ብሎት ነበርና ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ “የኤልያስን ጌታ ኤልያስ ነው ይልሃል? እግዚአ ኤልያስ፤ አምላከ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ” ሲል በደብረ ታቦር ተገኘ፡፡ ታያለህ የተባለው ሙሴም አየ፣ ትመሰክራለህ የተባለው ኤልያስም መሰከረ፡፡

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ “ጌታ ሆይ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው” ሲል ተደምጧል፡፡ ቃል በቃል ስናየው ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታ ሆይ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ማለቱ “አንተ እያበላኸን እየፈወስከን፣ ሙሴ እነዚህ መከራ ያደርሱቡኛል ይገድሉኛል ያልካቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያን እንዳይመጡ በደመና እየጋረደ፣ ቢመጡም አልያስ እሳት እያዘነመ እያባረራቸው በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ሲሆን ምሥጢራዊው መልእክቱ ግን “የኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት በሚታመንበት፣ ወልድ ዋሕድ በምትለው ሃይማኖት መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ ሰይጣን ድል በተደረገባት በታቦር ተራራ ምሳሌም በምትሆን በወንጌል ሕይወት፣ በቤተ ክርስቲያን መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ነው፡፡

ወቅቱ በሀገራችን የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ብርሃን የሚገለጥበት፣ ወገግታ የሚታይበት፤ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚሸጋገርበት ወቅት በመሆኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት እንዲሉ፡፡ እንዲሁም በዓለ ደብረ ታቦር ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት፤ ብርሃን የታየበትና ድምፀ መለኮቱ የተሰማበት ዕለት ስለሆነ ‘የብርሃን’ ወይም ‘የቡሄ’ በዓል ይባላል፡፡

በዚህ ሰሞን ልጆች የተገመደ ገመድ አዘጋጅተው ማጮሃቸው ሁለት ዓይነት ምስጢር የያዘ ትውፊታዊ ተግባር ነው፡፡ የመጀመሪያው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ግርፋቱንና ሞቱን እናስብበታለን፡፡ ሁለተኛው ደግሞ፤ ጅራፍ ሲጮህ እንደሚያስደነግጥ ሁሉ ከጌታ ጋር የነበሩት ሦስቱ ደቀ መዛሙርትም አብ በደመና ሆኖ ሲናገር መደንገጣቸውንና መውደቃቸውን የሚያስታውስ ነው፡፡ ድምፁን ስንሰማ የባሕርይ አባቱን የአብን ምስክርነት ቃል፤ እንደ ነጎድጓድ ድምፅ ያስታውሰናል፡፡

እናቶችም ለዚህ በዓል የሚሆን ዳቦ ለመጋገር ስንዴያቸውን ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉ ይሰነብታሉ፡፡ በበዓሉ ዋዜማ (ነሐሴ ፲፪ ቀን) ሕፃናት በየቤቱ እየዞሩ ቡሄ በሉ፤ ቡሄ መጣ፤ ያ መላጣ፤ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ … እያሉ ይጫወታሉ፡፡ በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ እያነሡ ይሰጧቸዋል፡፡ ለምን ሙልሙ ዳቦ ተዘጋጅቶ ለልጆች ይሰጣቸዋል ስንል፡- ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዕለት እረኞች ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል፡፡ ‘ቡሄ’ ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና በበዓሉ ችቦ የሚበራውም ከዚህ ታሪክ በመነሣት ነው፡፡

ጌታችን በፊታቸው ተለወጠ፤ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ

ሦስቱ ሐዋርያትና ሁለቱ ነቢያቱ በተራራው ሳሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሲጸልይ ሳለ መልኩ በፊታቸው ተለወጠ፡፡ ፊቱም እንደ ፀሐይ ብሩህ ሆነ፡፡ ልብሱም እንደ በረድ ጸዓዳ ሆነ፡፡ ጌታችን “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” እንዳለ የሕይወት ብርሃን፣ የሰው ልጆች ተስፋ የሆነውን ብርሃኑን ገለጠ፡፡ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብትንም ብርሃን ያለበሰ እርሱ ነው፡፡ ለመላእክት፣ ለጻድቃን ለቅዱሳን ሁሉ የጽድቅ ብርሃንን ያደለ የማይጠፋ ብርሃን እርሱ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ተራራ ብርሃነ መለኮቱን ገለጠ፡፡ ይህ ሁሉ ነገረ ተዋሕዶን እንዲረዱ የተደረገ መገለጥ ነው፡፡ ሰውነቱን አልካዱም፣ አምላክነቱን ግን ተጠራጥረው ነበርና አምላክነቱን ገለጠላቸው፡፡  

ቅዱስ ጴጥሮስም የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፊቱ ብሩህ መሆን፣ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ መሆን እንደዚሁም የቅዱሳን የነቢያት መምጣት እና ከጌታችን ጋር መነጋገራቸውን ከሰማ በኋላ “እግዚኦ እግዚእ ሠናይ ለነ ኃልዎ ዝየ፤ ጌታ ሆይ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው“ አለ፡፡ ቅዱሳን ነቢያቱ የወትሮ ሥራቸውን እየሠሩ ማለትም ሙሴ ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላት እያስገደለ፤ ኤልያስም ሰማይ እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናመ እያቆመ፤ አንተም አምላካዊ የማዳን ሥራን እየሠራህ ገቢረ ተአምራትህን እያሳየህ፤ በዚህ በተቀደሰ ቦታ በደብረ ታቦር መኖር ለእኛ እጅግ መልካም ነው” አለ፡፡ አምላካዊ ፈቃድህስ ከሆነ በዚህ ተራራ ላይ አንድ ለአንተ፤ አንድ ለሙሴ፤ አንድ ለኤልያስ ሦስት ዳስ እንሥራ ብሎም ጠየቀ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ “በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” ሲል ጌታችን በተአምራቱ ሲራቡ እያበላቸው፣ ሲጠሙ እያጠጣቸው፣ ሲታመሙ እየፈወሳቸው፣ ቢሞቱ እያነሣቸው፤ ሙሴም እንደ ቀድሞው ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላትን እየገደለ፤ ኤልያስ ደግሞ ሰማይን እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናም እያቆመ በደብረ ታቦር ለመኖር መሻቱን ያመለክታል፡፡ ዳግመኛም “ሦስት ጎጆ እንሥራ፤ አንዱን ለአንተ፤ አንዱን ለሙሴ፤ አንዱን ለኤልያስ” በማለት የእርሱንና የሁለቱን ሐዋርያት ጎጆ ሳይጠቅስ አርቆ መናገሩ በአንድ በኩል ነቢያቱን አስቀድሞ ባልንጀሮቹ ሐዋርያትን አለመጥቀሱ ትሕትናው ትሕትናውን፤ እንደዚሁም ከጌታችን ጋር ለመኖር ያለውን ተስፋ ያመለክታል፡፡  

የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ሲናገር ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፡፡ በደመናም “ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ፤ ልመለክበት የወደድኩት ለምስጢረ ተዋሕዶ የመረጥኩት የምወደው፣ የምወልደው ልጄ ይህ ነው እርሱንም ስሙት” የሚል ቃል መጣ፡፡ በዚህም የሥላሴ ምስጢር ለዓለም ተገለጸ፡፡ እግዚአብሔር አብ በደመና ሆኖ “የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው” እያለ፣ እግዚአብሔር ወልድ ሥጋን ተዋሕዶ ፍጹም አምላክ ሲሆን ፍጹም ሰውም ሆኖ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በነጭ ደመና ተመስሎ ተገልጸዋል፡፡ ስለዚህም ደብረ ታቦር ጌታችን ብርሃነ መለኮቱ፣ ክብረ መንግሥቱ የገለጠበት እንዲሁም የሥላሴ አንድነትን ሦስትነት የተገለጠበት ነው ብላ ቤተ ክርስቲያናችን ታስተምራለች፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መምህር አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ .ም፣ ገጽ ፫፻፲፭፫፻፲፯፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ ፳፻፯ .ም፣ ገጽ ፻፲፩፡፡       

ክረምትና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ለመደበኛው ትምህርት ራሳቸውን በማዘጋጀት በውጤት ታጅበው ለሚቀጥለው ዓመት ለመሸጋገር አቅማቸውን ሁሉ ተጠቅመው ጊዜአቸውን ሰጥተው ሲተገብሩ ማየት የተለመደ ነው፡፡ “የሚተክልም የሚያጠጣም አንድ ናቸው፤ ሁሉም እንደ ድካማቸው ዋጋቸውን ይቀበላሉ” (፩ኛ ቆሮ. ፫፥፰) ተብሎ እንደተጻፈው ድካሙ ብዙ ነው፡፡ ነገር ግን በራስ ጥረት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔርም ፈቃድና ድጋፍ እንደሚያስፈልግ መረዳት ይገባል፡፡ “እኔ የወይን ግንድ ነኝ፤ ቅርንጫፎቹም እናንተ ናችሁ፤ በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ ብዙ ፍሬ የሚያፈራ እርሱ ነው፤ ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና፡፡” (ዮሐ. ፲፭፥፭) በማለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደነገረን ከእርሱ ጋር መሆን ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔርን የሚፈልግ ልብ በፍሬ ይታጀባልና፡፡

በወጣትነት ለሥጋዊው ሕይወት መውጣት መውረድ እንደለ ሆኖ ለመንፈሳዊው ሕይወትም ጊዜ መስጠት፣ በጸሎት መትጋት፣ በንስሓ መመላለስ፣ ከበጎ ነገር ጋር መተባበር ከአንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን የሚጠበቅ ጉዳይ ነው፡፡ ሥጋን ብቻ ለማስደሰት በመሮጥ መንፈሳዊ ምግብ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል ብንዘነጋ ምን እናተርፋለን? ስለዚህ ወጣቶች (የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች) ለመንፈሳዊ ሕይወታችው ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጡና በመንገዱም ሊመላለሱ ይገባል፡፡

በወጣትነት ዘመን ስሜታዊነት የሚንጸባረቅበት ጊዜ ነው፡፡ ይህን ጊዜ በጥበብና በማስተዋል ማለፍ ካልተቻለ ለተለያዩ ክፉ ሥራዎች (ሱሶች፣ እግዚአብሔርን መርሳት፣ በጎ ነገርን አለማድረግ፣ …) መጋለጥን ያስከትላል፡፡ በተለይም እግዚአብሔርን አለማሰብ እንደ ቃሉም አለመመላስ በቀሪው ሕይወታቸው የሚያሳድረው ተጽእኖ ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን ዐስብ” (መክ. ፲፪፥፩) አንዲል በወጣትነት ፈጣሪን መፈለግ ይገባል፡፡ ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን ከሕፃንነት ጀምሮ በሰንበት ት/ቤት እንዲታቀፉ፣ የእግዚአብሔርንም ቃል እየተማሩ እንዲያድጉ የምታደርገው፡፡  

ማኅበረ ቅዱሳንም አገልግሎቱን በግቢ ጉባኤት ላይ በማተኮር ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ላይ በመሥራት የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል፡፡ ለተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው በተጓዳኝ መንፈሳዊ ትምህርትን በማስተማር፣ ሕይወታቸውን እንዲፈትሹ፣ ውጤታማም ሆነው እንዲወጡና በኦርቶዶክሳዊ እምነታቸው እንዲጸኑ ከፍተኛ ጥረት ያደርጋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችም የቀሰሙትን መንፈሳዊ ዕውቀትና ሕይወት ወደ ተግባር ለመለወጥ የሚረዳቸው ጊዜ ቢኖር በክረምቱ ወራት ትምህርት ተዘግቶ ወደ ቤተሰቦቻቸው ለዕረፍት ሲሄዱ ነው፡፡ በዚህ ወቅት የዕረፍት ጊዜያቸውን በአግባቡ ሊጠቀሙበት ይገባል፡፡ ዕረፍት ላይ መሆናቸው ሊያዘናጋቸው ስለሚችል አገልግሎቱ ላይ በማተኮር ራሳቸውን እንዲጠብቁ በአጥቢያቸው በሚገኝ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ በመሳተፍ እንደተሰጣቸውም ጸጋ ማገልገል፣ ዕውቀታቸውን ማካፈል፣ ለሌችም አርአያ መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡  

ሌላው በክረምት ወቅት የግቢ ጉባኤት ተማሪዎች ሊያደርጉት የሚገባው በተለያዩ በጎ አድራጎት ሥራዎች ላይ በመሳተፍ በተሰጣቸው ዕውቀት፣ ገንዘብና ጉልበት የተቸገሩትን በመደገፍ ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ዕረፍት ላይ መሆናቸው በርካታ በጎ ሥራዎችን ለመሥራት ዕድሉን ይፈጥርላቸዋል፡፡ “ለሥራ ከመትጋት አትስነፉ፤ በመንፈስ ሕያዋን ሁኑ፤ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ ለጸሎት ትጉ፡፡ በችግራቸው ቅዱሳንን ለመርዳት ተባበሩ፤ እንግዳ መቀበልንም አዘውትሩ” (ሮሜ. ፲፪፥፲፩-፲፬) በማለት እንደተነገረና ክረምቱ ምቹ ጊዜ በመሆኑ መትጋት ይገባል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሌላው በክረምት ወቅት ሊያደረጉት የሚገባቸው ነገር ቢኖር ለአብነት ትምህርት ትኩረት ሰጥተው ይማሩ ዘንድ ነው፡፡ አንዳንድ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የመደበኛ ትምህርቴን በደንብ እንዳልከታተል እንቅፋት ይሆንብኛል እያሉ በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠውን የአብነት ትምህርት ከመማር ችላ የሚሉ አሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ግን  ጊዜን መድቦ በዕቅድ ራስን ካለመምራት ጋር የሚመነጭ በመሆኑ ሲሸሹ ይታያሉ፡፡  ነገር ግን አጠገባቸው ያሉት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ጊዜአቸውን በአግባቡ በመጠቀም የአብነት ትምህርትን በመማር ለክህነት ሲበቁ እንመለከታለን፡፡ ስለዚህ በመንፈሳዊው ሕይወት ራስን ለማሳደግና በጎደለው ቦታ በመሙላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል በአጥቢያቸው በሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ወይም አቅራቢያቸው ባለ አብነት ትምህርት ቤት ገብተው መንፈሳዊውን ትምህርት መማር ይጠበቅባቸዋል፡፡

የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በክረምቱ ሰፊ ጊዜ ስለሚኖራቸው ሳይዘናጉ ከሌሎች በጎ አድራጎት ሥራዎችና አገልግሎት በተጓዳኝ ለሚቀጥለው ዓመት ትምህርታቸው የሚያግዟቸውን መጻሕፍት በመመርመር ለአዲሱ ዓመት ትምህርት ራሳቸውን ማዘጋጀትም ይገባቸዋል፤ ካለ ንባብ የሚያሳልፉት ቀን ሊኖር አይገባምና፡፡

በአጠቃላይ በክረምት የዕረፍት ወቅት እንደመሆኑ በመዝናናትና በስንፍና በመመላለስ የገነቡትን መንፈሳዊ ሕይወት ችላ እንዳይሉ ጥንቃቄ በማድረግ ባላቸው ጊዜ ራሳቸውንና ሌሎችን በመርዳት ከበረከቱ እንዲሳተፉ ያስፈልጋል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ፅንሰታ ለማርያም

ቅደስት ቤተ ክርስቲያናችን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችበትን ዕለት ነሐሴ ፯ ቀን በየዓመቱ በድምቀት ታከብረዋለች፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላጆች በእናቷ ሐና በኩል ቅድመ አያቶቿ ጴጥሪቃና ቴክታ ደጋጐችና እግዚአብሔርን የሚፈሩና በፍጹም ልቡናቸው እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ነበሩ፡፡

እግዚአብሔርን ማምለክ ብቻ ሳይሆን በባለጠግነታቸውም የታወቁ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ልጅ ስላልነበራቸው በጣም ያዝኑና ይተክዙ ስለነበር አንድ ቀን ጰጥሪቃ የሀብቱን ብዛት ተመልክቶ ሚስቱን (ቴክታ)ን “ያለን ገንዘብና ንብረት እንኳን ለእኛ ለልጅ ልጆቻችን የሚተርፍ ነው፡፡ ነገር ግን ወራሽ ልጆች የሉንም” እያለ በትካዜ ተናገራት፡፡ ቴክታም ከእርሷ ልጅ ባለመውለዱ ሌላ ወላድ ሴት የፈለገ መስሏት ‘እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ነውና ሌላ አግብተህ ወለድ” አለቸው በትካዜ ውስጥ ሆና፡፡  

ጴጥሪቃም “ይህንንስ በልቤ እንዳላሰብኩና እንዳልተመኘሁ እግዚአብሔር ያውቃል” በማለት ተናገራት፡፡ ቴክታም በሐዘን ወስጥ ሆና ሳለች ራእይ ታያለች፤ ነጭ እንቦሳ ከማሕኅፀኗ ስትወጣ፤ እንቦሳዪቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ሰባት ስትደርስ፣ ሰባተኛዋ ጨረቃን ስትወልድ፤ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ አየች። እርሷም ባየችው ራእይ ተገርማ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ አደነቀች፡፡ “በሕልሜ ነጭ ጥጃ ከማኅፀኔ ስትወጣ፣ ያችም ነጭ ጥጃ ደግሞ ነጭ ጥጃ ስትወልድ፣ እንደዚህ እየሆነ እስከ ሰባት ትውልድ ሲደርሱ ሰባተኛዪቷም ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋ ደግሞ ፀሐይን ስትወልድ አየሁ” በማለት አስረዳችው።

ጰጥሪቃም ባለቤቱ ባየችው ራእይ ተደንቆ ሕልም ለሚፈታ ሰው የሚስቱን ራእይ ተናገረ፡፡ ሕልም ተርጓሚውም ምስጢር ተገልጾለት “ሰባት አንስት ጥጆች መውለዳችሁ ሰባት ሴቶች ልጆች ይወለዳሉ፤ ነጭ መሆናቸው ደጋጎች ልጆች መሆናቸውን ሲያመለክት፤ ሰባተኛዪቱ ጨረቃን መውለዷ ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ናት፤ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም” በማለት ተረጐመለት፡፡ ጰጥሪቃም በተተረጎመለት ራእይ ተገርሞ ለሚስቱ ነገራት፤ እርሷም “የእስራኤል አምላክ የሚያደርገውን እርሱ ያውቃል” በማለት ፈጣሪዋን አመሰገነች፡፡

ቴክታ ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ሔሜን አሏት፤ ሔሜን – ዴርዴን ወለደች፤ ዴርዴም – ቶናን፤ ቶናም – ሲካርን ወለደች፤ ሲካርም – ሴትናን፤ ሴትናም – ሔርሜላን ወለደች፤ ሔርሜላም የተከበረችና የተመረጠች ዓለሙን ሁሉ ለፈጠረ ጌታ አያት ለመሆን የበቃችውን ሐናን ወልዳለች። ሐና በመልካም አስተዳደግ አድጋ አካለ መጠን ስታደርስ ከነገደ ይሁዳ ከመንግሥት ወገን የተወለደ የቅስራ ልጅ የአልዓዛር የልጅ ልጅ ከሚሆን ከኢያቄም ጋራ አጋቧት፡፡ ሁለቱም ወደ ቤተ እግዚአብሔር ዕለት ዕለት በመሄድ ለዐይናቸው ማረፊያ ለልባቸው ተስፋ የሚሆን ልጅ እንዲሰጣቸው ይለምኑ ነበር፡፡

ከዕለታት በአንደኛው ቀን ሁለቱም ወደ ቤተ እግዚአብሔር ሄደው ሲጸልዩ ውለው ሲመለሱ ርግቦች ከልጆቻቸው ጋር ደስ ብሏቸው ሲጫወቱ አይተው ሐና “አቤቱ ጌታዬ ግዕዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሣኸኝ?” ብላ ምርር ብላ አለቀሰች፡፡ ወዲያው ሳይውሉ ሳያድሩ ሱባኤ ይገባሉ፤ ኢያቄም ወደ በረሃ ሄዶ ሲጸልይ ሐና ደግሞ በቤቷ ዙሪያ ባለው የአትክልት ቦታ ሱባኤ ያዘች፤ በሱባኤያቸው ፍጻሜም ሁለቱም ራእይ አይተው ተነጋግረዋል፡፡

ኢያቄም “ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ብሎ የተገለጸለትን ለሐና ነግሯታል፤ ይኸውም የራእዩ ምስጢር፡- ወፍ የተባለው አካላዊ ቃል ክርስቶስ ሲሆን፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባሕርዩ ነው፤ ከላይ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ማለቱ የኢያቄምን ባሕርይ ባሕርይ እንደሚያደርግ ሲያጠይቅ ሲሆን፤ ሰባቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ምልአቱ፣ ስፍሐቱ፣ ርቀቱ፣ ልዕልናው፣ ዕበዩ ናቸው፡፡

ሐናም ተገልጾላት ለባሏ “ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ” አለችው። ምስጢሩም፡- ርግብ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትሆን፤ ነጭነቷ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ዘላለማዊ ድንግልናዋ ነው፤ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ ወደ ዦሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በዦሮዋ ሰምታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን የምትፀንሰውን ንጽሕት ርግብ የተባለችውን እመቤታችንን የምትወልድ መሆኗን ሲያጠይቅ ነው፡፡

ኢያቄምና ሐናም ይህንን ራእይ ሐምሌ ፴ ቀን ካዩ በኋላ “ወንድ ልጅ ብንወልድ ወጥቶ ወርዶ ይርዳን አንልም ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ይሆናል፤ ሴትም ብንወልድ ለቤተ እግዚአብሔር መጋረጃ ፈትላ ትኑር” ብለው ስእለት ከተሳሉ በኋላ ራእይ አየን ብለው ዕለቱን አልተገናኙም፤ አዳምንና ሔዋንን “ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሏት” ብሎ የተናገረው አምላክ ለእኛም ይግለጽልን ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ ሰባት ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ።

ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን “ከሰው የበለጠች ከመላእክት ሁሉ የከበረች ልጅ ትወልዳላችሁ” ብሎ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለሐና ነግሯት በፈቃደ እግዚአብሔር በብሥራተ መልአክ እመቤታችን ነሐሴ ሰባት ቀን እሑድ ተፀንሳለች፡፡ ለዓለም ሁሉ የድኅነት መገኛ የሆነች ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችበት ዕለት ነሐሴ ሰባት የተባረከች እንደመሆኗ መላው ክርስቲያን በዓሏን ሊያከብር ይገባል፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በከበሩ ኢያቄምና ሐና ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸው ከእኛ ጋር ይኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ከመጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ነሐሴ

       መጋቤ ሐዲስ ዶ/ር ሮዳስ ታደሰ፣ ነገረ ማርያም በሐዲስ ኪዳን

የጾመፍልሰታየዕለታትምንባባት፣ ምስባክ፣ ወንጌልና ቅዳሴ

ነሐሴ ፩

ምንባባት

. ፩ኛጢሞ. ፭ ፥፲፩

. ፩ኛዮሐ. ፭፥ ፩-፮

. ግብ.ሐዋ. ፭ ፥፳፯-፴፬

ምስባክ

. ወእነግር ስምዐከ በቅድመ ነገሥት ወኢትይኀፈር፤

ወአነብብ ትእዛዘከ ዘአፍቀርኩ ጥቀ፤

ወአነሥእ እደውየ ኀበ ትእዛዝከ ዘአፈቅር

ወንጌል

. ዮሐ. ፲፱፥፴፰-ፍጻሜ

ቅዳሴ 

. ዘዮሐንስ አፈወርቅ አው ዘእግዝእትነ

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛጢሞ. ፪፥፰-ፍጻሜ 

. ፩ኛጴጥ. ፫፥፩-፮

. ግብ.ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

ምስባክ

. ወይወስዱ ለንጉሥ ደናግለ ድኅሬሃ፤

ወቢጻሂ ይወስዱ ለከ፤

ወይወስድዎን በትፍሥሕት ወበሐሤት፤

ወንጌል 

. ዮሐ. ፰፥፱-፲፪

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛተሰ. ፩፥፩-ፍጻሜ

. ፩ኛ ጴጥ. ፫፥ ፲-፲፭

. ግብ. ሐዋ. ፲፬፥፳-ፍጻሜ

ምስባክ

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤

ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤

ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፤

ወንጌል 

. ሉቃ. ፲፰፥፱-፲፰

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ሮሜ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ

. ፩ ጴጥ. ፭፥፲፪

. ሐዋ. ፲፯፥፳፫-፳፰

ምስባክ

. እግዚኦ በኃይልከ ይትፌሣሕ ንጉሥ፤

ወብዙኃ ይትሐሠይ በአድኅኖትከ፤

ፍትወተ ነፍሱ ወሀብኮ፡፡

ወንጌል 

. ሉቃ. ፲፬፥፴፩-ፍጻሜ

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘቄርሎስ

ነሐሴ

ንባባት

. ፪ኛቆሮ. ፲፪፥፲-፲፯

. ፩ኛዮሐ. ፭፥፲፬-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፲፭፥፩-፲፫

ምስባክ

. ወትሰይመኒ ውስተ ርእሰ ሕዝብ፤

ሕዝብ ዘኢየአምር ተቀንየ ሊተ፤

ውስተ ምስማዐ ዕዝን ተሠጥዉኒ፤

ወንጌል

. ሉቃ. ፲፭፥፩-፲፩

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፫፥፲-፳፪

. ፩ኟ ጴጥ. ፫-፯

. ግብ.ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

ምስባክ

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤

ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤

ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፡፡

ወንጌል

. ማር. ፲፮፥፱-፲፱

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ

ምንባባት

. ዕብ. ፩፥፩-፲፯

. ፩ኛጴጥ. ፪፥፯-፲፰

. ግብ.ሐዋ. ፲፥፩-፴

ምስባክ

. ብፁዕ ብእሲ ዘአንተ ገሠጽኮ እግዚኦ፤

ወዘመሀርኮ ሕገከ፤

ከመ ይትገኀሥ እመዋዕለ እኩያት፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፲፮፥፲፫-፳፬

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

ሮሜ. ፱፥፳፬- ፍጻሜ

፩ኛጴጥ. ፬፥፲፪-ፍጻሜ  

ግብ. ሐዋ. ፲፮፥፴፭-ፍጻሜ

ምስባክ

. ወድቀት እሳት ወኢርኢክዋ ለፀሐይ፤

ዘእንበለ ይትዐወቅ ሦክክሙ ሕለተ ኮነ፤

ከመ ሕያዋን በመዓቱ ይውኅጠክሙ፡፡

ወንጌል

. ማቴ. ፯፥፲፪-፳፮

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፊልጵ. ፩፥፲፪-፳፬

. ፪ኛዮሐ. ፩፥፮-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፲፭፥፲፱-፳፭

ምስባክ

. ወትቀውም ንግሥት በየማንከ፤

በአልባሰ ወርቅ ዑፅፍት ወሑብርት፤

ስምዒ ወለትየ ወአጽምኢ እዝነኪ፡፡

ወንጌል 

. ዮሐ. ፲፥፩-፳፪

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘባስልዮስ

ነሐሴ ፲
ምንባባት

. ዕብ. ፲፪፥፳፪- ፍጻሜው 

. ፩ኛጴጥ. ፩፥፮-፲፫ 

. ግብ.ሐዋ. ፬፥፴፩-፳፭ 

ምስባክ

. ተዘከር ማኅበረከ በትረ ርስትከ፤

ወአድኀንከ በትረ ርስትከ፤
ደብረ ጽዮን ዘኀደርከ ውስቴታ፡፡

ወንጌል

. ሉቃ. ፲፮፥፱-፲፱ 

ቅዳሴ 

ዘእግዝእትነ ማርያም 

ነሐሴ ፲፩
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፭፥፲፩-ፍጻሜ  

. ፩ኛዮሐ. ፪ ቊ. ፲፬-፳ 

. ግብ. ሐዋ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜው 

ምስባክ

. ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ፤

ወትሠይሚዮሙ መላእክተ ለኵሉ ምድር፤
ወይዘክሩ ስመኪ በኵሉ ትውልደ ትውልድ፡፡

ወንጌል

.ሉቃ. ፮፥፳-፳፬ 

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ ፲፪
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፱፥፲፯-ፍጻሜ

. ይሁዳ. ቊ. ፰-፲፬ 

. ግብ.ሐዋ. ፳፬፥፩-፳፪ 

ምስባክ

. እግዚኦ ኩነኔከ ሀቦ ለንጉሥ፤

ወጽድቀከኒ ለወልደ ንጉሥ፤
ከመ ይኰንኖሙ ለሕዝብከ በጽድቅ፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፳፪፥፩-፲፭ 

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ

ነሐሴ ፲፫
ምንባባት

. ዕብ. ፲፩፥፳፫-፴ 

. ፪ኛጴጥ. ፩፥፲፭ 

. ግብ.ሐዋ. ፯፥፵፬-ፍጻሜ

ምስባክ

. ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ፤

ወይሴብሑ ለስምከ፤
መዝራዕትከ ምስለ ኃይል፡፡

ወንጌል 

. ሉቃ. ፱፥፳፰-፴፰ 

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዲዮስቆሮስ፡፡

ነሐሴ ፲፬
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፩፥፲-፲፪ 

. ያዕ. ፩፥፲፪ 

. ግብ.ሐዋ. ፲፥፴-፵፬ 

ምስባክ

. ዘአዘዝከ መድኃኒቶ ለያዕቆብ፤

ብከ ንወግዖሙ ለኵሎሙ ፀርነ፤
ወበስምከ ናኃሥሮሙ ለእለ ቆሞ ላዕሌነ፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፲፯፥፲፬-፳፬ 

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ

ነሐሴ ፲፭

ምንባባት        

. ፩ኛቆሮ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ   

. ይሁዳ. ፩፥፲፯-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፩፥፲፪-፲፭

ምስባክ   

. ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ፤

ቅዳሴ፡      

. ዘሐዋርያት

ነሐሴ ፲፮

ምንባባት       

. ሮሜ. ፰፥፴፩-ፍጻሜ   

. ዮሐ. ፪፥፩—፯  

. ግብ.ሐዋ. ፩፥፲፪-፲፭

ምስባክ፡   

. ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል፤

እግዚአብሔር ውስተ ማዕከላ ኢትትሐወክ፤

ወይረድኣ እግዚአብሔር ፍጽመ፡፡

ወዓዲ ወተዚያነዉ ዳኅናሃ ለኢየሩሳሌም፤

ወፍሥሐሆሙ ለእለ ያፈቅሩ ስመከ፤

ይኩን ሰላም በኃይልከ፡፡

ወንጌል

. ማቴ. ፳፮፥፳፮-፴፩

ቅዳሴ      

. ዘእግዚእነ

ጾመ ፍልሰታ ለማርያም

እንኳን ለፍልሰታ ለማርያም ጾም በሰላም አደረሳችሁ!

ጾመ ፍልሰታ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከደነገገቻቸው ሰባቱ የዐዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡ ይህንንም ጾም ከነሐሴ ፩-፲፮ ቀን ድረስ ለሁለት ሱባኤ ከሰባት ዓመት ሕፃናት ጀምሮ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ የሚጾሙትና በናፍቆት የሚጠበቅ ጾም ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያትን አብነት አድርጋ የምትጾመው ጾም እንደመሆኑ ምእመናን በየገዳማቱና አድባራት በመገኘት ራሳቸውን ለእግዚአብሔር በማስገዛት በሱባኤ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደትና በምሕላ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ያገኙ ዘንድ በፍጹም ፍቅርና ትጋት ይጾሙታል፡፡  

ፍልሰታ የሚለው ቃል “ፈለሰ” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም “መለየት፣ ማረግ፣ ወደ ላይ መውጣት፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መሄድ” ማለት ነው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በ፷፬ ዓመቷ ከዚህ ዓለም ድካም ጥር ፳፩ ቀን ፵፱ ዓ.ም በማረፏ  ሐዋርያት ሥጋዋን በጌቴሴማኒ ለማሳረፍ ሲወስዷት አይሁድ “እንደ ልጇ ተነሣች፤ ዐረገች እያሉ እንዳያውኩን በእሳት እናቃጥላት” ብለው በዓመፃ ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም በክፋት ተነሣስቶ አጎበሩን ይዞ ሊያወርዳት ሲል የእግዚአብሔር መልአክ ሁለት እጆቹን ቆረጠው፡፡ እግዚአብሔርም ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ እመቤታችንን በደመና ነጥቆ  ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡ ዮሐንስም በዕፀ ሕይወት ላሉት ነፍሳት “ዛቲ ይእቲ ሕይወትክሙ ኪያሃ ሰብሑ፤” ብሎ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ተቀብለው “ብፅዒት ከርስ እንተፆረትኪ ወብፅዓት ዓይንት እለእርያ ኪያኪ ፤ ሕይወታችሁ ይህቺ ናት፤ እርሷን አመስግኑ፣ አንቺን የተሸከመች ማኅፀን የተባረከች ናት፤ አንቺን ያዩ ዓይኖችም የተባረኩ ናቸው ፤” ብለው አመስግነዋታል፡፡ “ትውልድ ዘኢይሀልፍ ያመሰግኑኛል” ማለት ይህ ነው፡፡  

ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ሐዋርያቱ በተመለሰ ጊዜ ሐዋርያቱ “እመቤታችንስ?” እያሉ በጥያቄ አፋጠጡት፡፡ እርሱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገነት በዕፀ ሕይወት እንዳስቀመጣት ነገራቸው፡፡ እነርሱም ዮሐንስ ያየውን እኛም ማየት አለብን ብለው ከነሐሴ ፩-፲፬ ሱባኤ ገቡ፡፡ ጌታችንም የሐዋርያቱን ጽናት ፍቅር ተመልክቶ የእመቤታችንን ትኩስ ሥጋ ከዕፀ ሕይወት አምጥቶ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ተቀብለው በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡ በሦስተኛውም ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ ሕንድ በደመና ተጭኖ ሲመጣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በመላእክቱ ታጅባ ስታርግ ተገናኙ፡፡ ሐዋርያው ቶማስም ሐዋርያት ያዩትን እኔ ሳላይ ብሎ አዘነ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?” በማለት ከደመናው ወደ መሬት ራሱን ሊጥል ሲቃጣው እመቤታችን ማረጓን እርሱ ብቻ እንደተመለከተ ነግራ የተገነዘችበትን ሰበን ሰጥታው ዐረገች፡፡  

ሐዋርያው ቶማስ ወደ ሐዋርያት በተመለሰ ጊዜም “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው፡፡ እነርሱም “አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆናል?” አላቸው፡፡ ከሐዋርያት መካከል ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ በፊት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ ተጠራጥሮ እንደነበር በመግለጽ ገሰጸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ተቈጥቶ የእመቤታችንን ክቡር ሥጋ ለቅዱስ ቶማስ ለማሳየት ሔዶ መቃብሯን ቢከፍት የእመቤታችንን ሥጋ ሊያገኘው አልቻለም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ቆመ፡፡

ቅዱስ ቶማስም “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ስታርግ አግኝቻታለሁ” ብሎ የሰጠችውን ሰበን ለሐዋርያት ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት እየተደሰቱ ሰበኑን ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን በቅዳሴ ጊዜ ሠራዒ ዲያቆኑ በሚይዘው መስቀል ላይ የሚታሠረው መቀነት መሰል ልብስ፤ እንደዚሁም አባቶች ካህናት በመስቀላቸው ላይ የሚያደርጉት ቀጭን ልብስና በራሳቸው የሚጠመጥሙት ነጭ ሻሽ የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡

ሐዋርያትም ቶማስ ያየውን እውነት ለማየትና ከእመቤታችን በረከት ለማግኘት ከነሐሴ ፩-፲፮ በጾምና በጸሎት ተወስነው ቆይተዋል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታቸውን ሰምቶ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችንን መንበር፤ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፤ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ እመቤታችንንም ሐዋርያትንም አቍርቧቸዋል፡፡ እነርሱም እመቤታችንን በዓይናቸው ከማየት ባሻገር አብረው ሥጋውን ደሙን ተቀብለዋል /ትርጓሜ ውዳሴ ማርያም/፡፡ እንደ ልጇ እንደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ትንሣኤ” ያሰኘውም ይህ ታሪክ ነው፡፡

በጾመ ፍልሰታ በቤተ ክርስቲያናችን በየቀኑ በማኅሌቱ፣ በሰዓታቱና በቅዳሴው በሚደርሰው ቃለ እግዚአብሔር ነገረ ማርያም ማለትም የእመቤታችን ከመፀነሷ ጀምሮ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለው ታሪኳ፣ ለአምላክ ማደሪያነት መመረጧ፣ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ክብሯ፣ ርኅርራኄዋ፣ ደግነቷ፣ አማላጅነቷ፣ ሰውን ወዳድነቷ በስፋት ይነገራል፡፡ እመቤታችንን ከሚያወድሱ ድርሳናት መካከልም በተለይ ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከነገረ ማርያም ጋር በማዛመድ የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም፤ እንደዚሁም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌ (ከነገረ ክርስቶስ) እና ከነገረ ማርያም ጋር በማመሣጠር የሚያትተው ውዳሴ ማርያምም በስፋት ይጸለያል፤ ይቀደሳል፤ ይተረጐማል፡፡ በሰንበታት የሚዘመሩ መዝሙራት፤ በየዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለተዋሕዶ በእግዚአብሔር መመረጧን፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን፣ ክብሯን፣ ቅድስናዋን፣ ንጽሕናዋን የሚያወሱ ናቸው፡፡

ምእመናንም በረከት ያገኙ ዘንድ የዲያብሎስንም ፈተና ድል ይነሡ ዘንድ ከነሐሴ ፩-፲፮ ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው በየገዳማቱና በየአብያተ ክርስቲያናቱ በዓት አዘጋጅተው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው አስገዝተው ይጾማሉ፤ ይጸልያሉ፤ እንደዚሁም ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ይህ ጾም ለእመቤታችን ያለንን ፍቅር የምንገልጽበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ኦርቶዶክሳውያን ሕፃናት ከሌላው ጊዜያት በተለየ ሁኔታ ትምህርተ ወንጌል የሚማሩት፤ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሚቀበሉት በዚህ በጾመ ፍልሰታ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋና በረከት አይለየን፡፡

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፤

በሀገራችን በኢትዮጵያና በመላው ዓለም የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፡-

የክብር ባለቤት እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሰባት ዓ.ም የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ!

‹‹ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፤ ነፍሴ እግዚአብሔርን እጅግ ታከብረዋለች›› (ሉቃ. ÷፵፮)

ይህንን ዐረፍተ ነገር የተናገረችው ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በሠራው ስሥራ ሰውነታችንን ለመዋሐድ የመረጣት ምርጥ የፍጥረት ወገን ናት፤ ፍጥረት ሁሉ በእግዚአብሔር ለእግዚአብሔር ተፈጥሮአል፤ የእግዚአብሔርም ነው፤ የቅድስት ድንግል ማርያም መመረጥም በእግዚአብሔር ለሰው የተደረገ ምርጫ ነው፤

የሰው መዳን ከጥንቱ ከጠዋቱ በእግዚአብሔር ልዩ አሠራር እንደሚከናወን በነቢያት የተገለጸ ነበረ፣ ‹‹አኮ በተንባል ወአኮ በመልአክ አላ ለሊሁ እግዚእ ይመጽእ ወያድኅነነ፤ በአማላጅም አይደለም፤ በመልአክም አይደለም እሱ ራሱ ጌታ መጥቶ ያድነናል እንጂ›› የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ትንቢትም ይህንን ያስረዳል፤ ቃለ ትንቢቱ ድኅነታችን በጌታ ቤዛነት እንደሚከናወን ያረጋግጣል፤ ይህም ሊሆን የቻለው ከፍጡራን ወገን በደሙ ቤዛነት ፍጡራንን የሚያድን ስለሌለ ነው፤

ከዚህ አንጻር የሰው መዳን በእግዚአብሔር አሠራር በደም ቤዛነት ከሆነ፣ በደሙ ቤዛነትም ዓለምን ማዳን የሚችል ከፍጡር ወገን ከሌለ፣ መዳናችን በእግዚአብሔርና በእግዚአብሔር እጅ ብቻ የተንጠለጠለ ነበረ፤ እግዚአብሔር በደሙ ቤዛ ሆኖ ዓለምን ለማዳን ደግሞ ደም ሊኖረው ይገባ ነበር፤ በመሆኑም እግዚአብሔር በክዋኔው ደም የሌለው ስለሆነ ለቤዛ ዓለም የሚፈስ ደምን ገንዘብ ማድረግ ነበረበት፤ ይህንን ደም ለመዋሐድ ቅድስት ድንግል ማርያምን መረጠ፤ ለዚህ ብቁ እንድትሆንም በእስዋ ላይ ሥራውን ሥራ፤ በምርጫውም መሠረት ከቅድስት ድንግል ማርያም ደማዊ ሥጋንና ነፍስን ተዋሕዶ ለቤዛዊ መሥዋዕት መንገዱን አመቻቸ፤

ቅድስት ድንግል ማርያም በነገረ ድኅነት መሰላል ለመሆን በእግዚአብሔር የተመረጠች በመሆኗ አንቀጸ አድኅኖ ወይም የድኅነት በር ትባላለች፤ ቅድስት ድንግል ማርያም ለዚህ ታላቅ ነገረ ድኅነት መመረጥዋ እጅግ ታላቅ ዕድል መሆኑን ስለተገነዘበች ‹‹ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና›› በማለት እግዚአብሔርን በመዝሙር አመስግናለች አክብራለችም፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

የቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና እና የአምልኮ መዝሙር የኛም መዝሙር ነው፤ እግዚአብሔር ለቅድስት ድንግል ማርያም ታላላቅ ሥራዎችን እንደሠራ ለኛም ብዙ ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልናል፤ እየሠራልንም ነው፤ ለሠራልን አምላክም እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም ታላቅ ክብርን መስጠት ይገባናል፤ ለእግዚአብሔር የምንሰጠው ክብርም በቃል ብቻ የሚገለጽ ሳይሆን በተግባር የሚታይ ሊሆን ይገባል፤ የድንግል ማርያም መንፈሳዊ ሕይወት በማስተዋል በትሕትና፣ በትዕግሥት በርኅራኄ በመታዘዝ በንጽሕና በቅድስና በክብርና በበረከት የተሞላ እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ከተጻፈው ሥነ ሕይወቷ መረዳት እንችላለን፤ ታድያ በእርሷ ክብርና ተማሕፅኖ የምንተማመን ልጆቿም የእሷን ያህል እንኳ ባንችል ወደ እርስዋ የሚጠጋጋ መንፈሳዊ ሕይወት ሊኖረን ይገባል፤ ይህም የምናደርገው ለእግዚአብሔር ክብርና ለእኛ መዳን ሲባል ነው፤ እኛ እግዚአብሔርን ስናከብር እንከብራለን እንድንማለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር የማንሰጥ ከሆነ ግን ውጤቱ መክበር ሳይሆን ሌላ ነው የሚሆነው፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

እኛ በየጊዜው ጾምን እንድንጾም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት ፈቃደ ሥጋችንን በመግራት ለእግዚአብሔር ታዛዦች እንድንሆን ነው፤ ጾም የኃጢኣት መግቻ መሣሪያ በመሆኑ ‹‹ልጓመ ኃጢኣት›› ተብሎ ይታወቃል፤ በዚህም ሰውነታችንን ለግብረ ኃጢአት ከሚያጋግሉ ምግቦች አርቀን በሰከነ መንፈስ እግዚአብሔርን እያሰብን ኃጢአታችንንም እያስታወስን በንስሓ ወደ እርሱ ለመቅረብና ለሱ ለመታዘዝ እንጾማለን፤

የጾም ጥቅም ከጥንት ጀምሮ የታወቀ በእግዚአብሔርና በሰውም ተቀባይነት ያለው ነው፤ እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ መታዘዝን ይወዳልና በጾምና በጸሎት ለሱ ልንታዘዝ ይገባል፤ እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ሊያድር የቻለው ‹‹እንዳልኸኝ ይሁንልኝ›› ብላ ታዛዥነትዋን በገለጸች ጊዜ ነው፤ እኛም እንዳልከን ይሁንልን እያልን እንደ እስዋ ታዛዥ መሆን አለብን፤

ዛሬ በዓለማችን ያለው መተረማመስ ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝ ያመጣው ጣጣ እንደሆነ ማንም አይስተውም፤ መታዘዙ ቢኖር ኖሮ የሰው ልጅ ሰውን የሚያድን ብቻ እንጂ ሰውን የሚገድል መሣሪያ አያመርትም ነበር፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ወንድምህን እንደ ራስህ አድርገህ ውደድ አለ እንጂ ግደል ብሎ አላዘዘምና ነው፤ አሁንም በዚህ ባለንበት ዓለም በጣም ተባብሶ የሚገኘው የመጠፋፋት ዝንባሌ ለእግዚአብሔር በመታዘዝ በሰላምና በሰጥቶ መቀበል ካልተቋጨ ዳፋው አስከፊ መሆኑ አይቀርም፤

ከዚህ አንጻር ዛሬም ለሰው ልጆች ሁሉ የምናስተላልፈው መልእክት ‹‹በፍቅር ከሆነ ትንሹም ለሁሉ ይበቃልና ያለውን በጋራ በመጠቀም በፍቅርና በሰላም እንኑር›› የሚል ነው፤ ‹‹ፍትሕና ርትዕም ለሰው ልጅ መነፈግ የበለትም፤ ሰው በምድር ላይ ሠርቶ የመኖር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፤ ይህንን ማድረግ ማለት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ማለት ነው፤ ስለሆነም ለእግዚአብሔር ክብርና ለራሳችን መዳን ስንል ለእርሱ በመታዘዝ በሕይወትና በሰላም እንኑር፡፡

በመጨረሻም፡

በጾመ ማርያም ሱባኤ ስለ ሀገር ሰላምና ስለ ሕዝብ ደኅንነት በመጸለይ፣ በልዩ ልዩ ምክንያት በመከራ ላይ ወድቀው የሚገኙ ወገኖቻችንን በሚያስፈልጋቸው ሁሉ በመርዳት ሱባኤውን እንድናሳልፍ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን እናስተላልፋለን፤

መልካም የሱባኤ ወቅት ያድርግልን፤ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

ነሐሴ 1 ቀን 2017 .

ዋሽንግተን ዲሲ

“እናቴ ሆይ ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ”

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ላይ ተመሥርታለችና ዙሪያዋን በከበቧት ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን መላእክት፣ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ተጋድሎና ጸሎት የታጠረች ናት፡፡ “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤ በተራራ ላይ የተሠራች ከተማ መሰወር አይቻላትም” (ማቴ. ፭፥፲፬) እንዲል መጽሐፍ ቅዱስ ቅዱሳንን በብርሃን ይመስላቸዋል፤ ቅዱሳን ወንጌልን በመስበክ ዓለምን አጣፍጠዋታልና፡፡

ቤተ ክርስቲያን ለእነዚህ ዓለምን ድል ለነሱ ቅዱሳን ከዓመት እስከ ዓመት የተወለዱበትን፣ ተአምራት ያደረጉበትንና ያረፉበትን ቀን አስልታ መታሰቢያቸውን በድምቀት ታከብራለች፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት መካከል ደግሞ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ንጉሡ ለሚያመልከው ጣኦት አንሰግድም በማለታቸው መከራ የተቀበሉበትና በእምነታቸው ጽናት እግዚአብሔርን ደስ በማሰኘታቸው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከነደደው እሳትና የፍላቱ ኃይል ዐሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደ ላይ ከሚዘል የፈላ ውኃ ያዳነበትን ቀን ሐምሌ ፲፱ ቀን አስባ በድምቀት ታከብራለች፡፡

በቤተ ክርስቲያን በየዕለቱ ከሚነበቡ መጻሕፍት መካከልም ስንክሳር ታሪኩን እንዲህ ይተርከዋል፡፡

ቅድስት ኢየሉጣ በሮም ግዛት በሚገኝ አንጌቤን በሚባል አገር በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በክርስትና ሃይማኖት እና በበጎ ምግባር ጸንታ ትኖር የነበረች ደግ ሴት ናት፡፡ በሥርዓት ያሳደገችው ቂርቆስ የሚባል የሦስት ዓመት ሕፃን ልጅም ነበራት፡፡ ይህቺ ቅድስት የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራቷ ከልጇ ጋር ከሮም ወደ ጠርሴስ በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡

የንጉሡ ወታደሮችም እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን አስፈራሯቸው፡፡ ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኃ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡

በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡

አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም “እናቴ ሆይ! ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ” እያለ ቅዱስ ቂርቆስ እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን እንድትጸና አበረታታት፡፡ የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡ እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አስነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲሆን፣ መኰንኑ በተአምራቱ ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡

ዳግመኛም በፈላ የጋን ውኃ ውስጥ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ፤አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ ከፈላ

 ውኃ ያድነናል እያለ ያረጋጋት፣ በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡

ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ውኃውን እንደ ውርጭ አቀዘቀዘው፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ አስገብተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል አድኗቸዋል፡፡ በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡

እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ እያለ በእሳት ውስጥ ሊጣሉ ባሉበት ወቅት እናቱን እንድትጸናና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ሁሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል አይዞህ! አይዞሽ! አትፍራ! አትፍሪ በመባባል በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ ታግሠን፣ እስከ ሞት ድረስ በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር ይገባናል፡፡

ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይሆን በጋራ ዋጋ የሚያገኙበት የድኅነት በር ነውና፡፡ ከዚሁ ሁሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን በተአምኖ ንሴፎ ትንባሌ ዚአከ መዓልተ ወሌሊተ፤ በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡ እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል” ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፴፬፥፯)፡፡ ይህን እንድናደርግም የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡ የቅዱስ ገብርኤል፣ ቅድስት ኢየሉጣ እና ቅዱስ ቂርቆስ ጸሎታቸውና ምልጃቸው ይጠብቀን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ