ማኅበረ ቅዱሳን የባለ ዕድለኞች ዕጣ ቁጥሮችን ይፋ አደረገ

ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎትን ለማጠናከር ይረዳው ዘንድ “ዘመኑን የዋጀ ንቁ ትውልድ ለቤተ ክርስቲያን” በሚል መሪ ቃል ለአባላት፣ ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና አገልግሎቱን ለሚደግፉ ምእመናን ሲያሠራጭ የቆየው ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም፣ ወደ ግብጽና ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝትን ጨምሮ ሌሎችንም ዕድሎችን የሚያስገኙት የበረከት የዕጣ ቁጥሮች በቴክኖሎጂ በታገዘ የዕጣ አወጣጥ መርሐ ግብር ታዛቢዎችና ምእመናን በተገኙበት ኅዳር ፳፩ ቀን ፳፳፻፲፰ ዓ.ም ይፋ አደረገ፡፡  

በዕጣ አወጣጥ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ መምህር ዋሲሁን በላይ ባስተላለፉት መልእክት “ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በተሻለ ጥራትና አቅም ለማስተማር ብቻውን ሳይሆን የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ፣ የሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የመምህራንና የምእመናን ትብብርና ድጋፍ ሳይለየው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በተሻለ ጥራትና አቅም አገልግሎቱን እየሰጠ ይገኛል” በማለት የገለጹ ሲሆን የበረከት ዕጣ ትኬቱን በማሠራጨት ሂደት ውስጥ የተሳተፉትን ሁሉ አመስግነዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ አበበ በዳዳ የበረከት ዕጣ ትኬቱ የተዘጋጀበት ምክንያትና ሂደቱን በተመለከተ ባስተላለፉት መልእክት “ማኅበረ ቅዱሳን ከ፲፱፻፹፬ ዓ.ም ጀርሮ በቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠው ፈቃድና ኃላፊነት መሠረት  የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ለማስተማር መምህራንን በመመደብ፣ መማሪያ ቦታን በማዘጋጀት፣ በንስሓ አባቶች አማካይነት ሕይወታቸውን በመንፈሳዊ መንገድ እንዲመሩ በማድረግ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ኦርቶዶክሰውያን ተማሪዎችን በማፍራት አስመርቋል፡፡ “በዚህም አገልግሎት ተማሪዎች ለራሳቸው፣ ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ አገልግሎት እያበረከቱ ይገኛሉ፡፡” ብለዋል፡፡

አቶ አበበ አያይዘውም “ማኅበረ ቅዱሳን ከ፲፱፩፺፮ ዓ.ም ጀምሮም ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ሲያስተምር በየጊዜው የሚታዩ ክፍተቶችን በማረም በ፳፻፮ ዓ.ም በዓለማችን፣ በሀገራችንና በቤተ ክርስቲያን በሚታዩ ተለዋዋጭ ሁኔታዎች፣ የሰ/ት ት/ቤቶች ከ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ሥርዓተ ትምህርት መዘጋጀት፣ ማኅበረ ቅዱሳን ከ፳፻፲፮ ዓ.ም የተቋማዊ ለውጥ ትግበራ መጀመርና የመንግሥት የትምህርት ፖሊሲ መቀያየር ከግምት ውስጥ በማስገባት ከዐሥር ዓመታት በኋላ በ፳፻፲፯ ዓ.ም ለግቢ ጉባኤያት ሲሰጠው የነበረውን ሥርዓተ ትምህርት ከግምት ውስጥ በማስገባት መከለስ ችሏል” ሲሉ ገልጸዋል፡፡

“እነዚህም ምክንያቶችን መሠረት በማድረግ ፲፬ የትምህርት ዓይነቶች የተዘጋጁ ሲሆን ለኅትመት፣ የመምህራንን አቅም፣ ጥራትና ቁጥር ለማሳደግ፣ የመማሪያ ቦታ ችግሮችን ለመቅረፍና የሥልጠና መስጫ መእከል ለመገንባት ታስቦ የበረከት ዕጣው ተዘጋጅቷል” በማለት አብራርተዋል፡፡

በበረከት ዕጣ ትኬቱ አቅማቸውን ሁሉ በመጠቀም ድጋፍ ላደረጉና በማሠራጨት ለተባበሩት አካላት ሁሉ ምስጋና በማቅረብ የዕጣ መውጣት መርሐ ግብሩ እንዲጀመር አድርገዋል፡፡ በዚህም መሠረት፡-

፩ኛ ዕጣ፡- 409652፡- ወደ ኢየሩሳሌሌም ገዳማት ጉዞ ለ፯ ቀናት፣  

፪ኛ ዕጣ፡- 309903፡- ወደ ግብጽ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝት ለ፯ ቀናት፣

፫ኛ ዕጣ፡- 076840፡- ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት ወደ አንዱ ከአንድ ቤተሰብ ጋር መንፈሳዊ ጉብኝነት በአውሮፕላን ለ፭ ቀናት፣

፬ኛ ዕጣ፡- 366930፡- ወደ ኢትዮጵያ ገዳማት መንፈሳዊ ጉብኝት ከሁለት ቤተሰብ ጋር በየብስ ትራንስፖርት ለ፯ ቀናት፣

፭ኛ ዕጣ፡- 160582፡- ላፕቶፕ ኮምፐዩተር core i7 10Th G የሚያስገኘው የዕጣ ቁጥር፣

፮ኛ ዕጣ፡- 201414፡- ላፕቶፕ ኮምፒዩተር core i5 የሚያስገኘው የዕጣ ቁጥር፣

፯ኛ ዕጣ፡- 478450፡- ሳምሰንግ ታብሌት ጋላክሲ (Samsung Galaxy tablet A8 10.5) ሆነው ወጥተዋል፡፡

በተጨማሪም ፳፩ የዳረጎት ዕጣዎች የወጡ ሲሆን ዐሥር የዕጣዎች እያንዳንዳቸው የሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ፤ እንዲሁም አሥራ አንድ ዕጣዎች እያንዳንዳቸው መዝሙረ ዳዊት የሚያስገኙ ሆነው ወጥተዋል፡፡  

በዚህም መሠረት የሰማንያ አሐዱ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስገኙት ዕጣዎች፡-

  • 373427
  • 360509
  • 345974
  • 249715
  • 263391
  • 435703
  • 320085
  • 394074
  • 315800
  • 232590

ዐሥራ አንድ የመዝሙረ ዳዊት የጸሎት መጽሐፍ የሚያስገኙት ዕጣዎች፡-

  • 374223
  • 354749
  • 247657
  • 265287
  • 317331
  • 435060
  • 319033
  • 291453
  • 179959
  • 259285
  • 244216 ሆነው ወጥተዋል፡፡

ኅዳር ጽዮን

በዓለ ሢመቱ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል

በዲ/ን አብርሃም

ኅዳር ፲፪ ቀን ንዑድ ክቡር የሆነ ለፍጥረቱ ሁሉ የሚማልድ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል የተሾመበት ዕለት ነው። የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍት “ኅዳር ፲፪ በዚህች ቀን ለሰው ወገን የሚያዝንና የሚራራ በእግዚአብሔር ጌትነት ፊት ሁል ጊዜ በመቆም ለፍጥረቱ ሁሉ የሚማልድ የመላእክት አለቃቸው ለሆነ ለቅዱስ ሚካኤል የበዓለ ሢመቱ መታሰቢያ ነው።” (መጽሐፈ ስንክሳር ኅዳር ፲፪፤ ድርሳነ ሚካኤል ዘኅዳር) በማለት ይገልጻሉ፡፡

ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‘ሚ’- ‘መኑ’፣ ‘ካ’- ‘ከመ’፣ ‘ኤል’- ‘አምላክ’ ማለት ሲሆን በአንድነት ሲነበብ “መኑ ከመ አምላክ፤ እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?” ማለት ነው። እግዚአብሔር መልእክትን በፈጠረ ጊዜ ሳጥናኤልን የመላእክት ሁሉ አለቃቸው አድርጎ ሹሞት ነበር። ነገር ግን ሳጥናኤል ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ክብር ትቶ አምላክነትን በመሻቱ በትዕቢቱ ምክንያት ሥልጣኑን ገፍፎ ወደ ጥልቁ ጥሎታል፤ በቦታውም ቅዱስ ሚካኤልን ሹሞታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህን ምክንያት በማድረግ ኅዳር ፲፪ ቀን በየዓመቱ በዓለ ሢመቱን ታክብራለች።

ደጉ እና ሩኅሩኁ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በስሙ ለተማጸንን ሁሉ ከእግዚአብሔር የሚያማልደን ምሕረትን የሚያሰጠን መልአክ ነው ”ተውህቦ ምሕረት ለሚካኤል” እንዲል (ሥርዓተ ቅዳሴ)። ቅዱስ ሚካኤል ለፍጥረታት ሁሉ የሚራዳና የሚያዝን በእግዚአብሔር ፊት የሚቆምልን የምሕረትና የሰላም መልአክ ነው። “በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል” (ዳን. ፲፪፥፩) ነቢየ እግዚአብሔር ዳንኤል ‎የቅዱስ ሚካኤልን ክብር ሲገልጥ ይህንን ብሎ ብቻ አልቀረም “ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ” በማለት እኛ የአዳም ልጆች ዲያብሎስ ባዘጋጀልን መሰናክል እንዳንወድቅ የሚረዳን መልአክ እንደሆነ ይናገራል፡፡ (ዳን. ፲፥፲፫)

“ቅዱስ ሚካኤል ሆይ የያሬድ ልጅ ሄኖክ እንደጻፈው። ከልዑል ስም አጠራር ጋር ለተባበረ ስም አጠራርህ ሰላም እላለሁ። የእግዚአብሔር የምክሩ አበጋዝ ሆይ የተቸገሩትን የተጨነቁትን ዘወትር እንደምትረዳቸው ሁሉ እኔንም ለመርዳት ክንፍህን ዘርግተህ ፈጥነህ ድረስልኝ።” በማለት የቅዱስ ሚካኤልን ተራዳኢነት ይገልጻል፡፡ (መልክአ ሚካኤል)

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት የቅዱስ ሚካኤልንና የሌሎች መላእክትን ክብርና አገልግሎት ሲገልጥ “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፥ ያድናቸውማል።”‎ (መዝ. ፴፫፥፯) እንዲል ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን በሚፈሩ ሰዎች ዙሪያ ሁል ጊዜ ይከባሉ፤ ከሰይጣን ፈተና፣ ከረኃብ፣ ከችግር፣ ከመከራ ሁሉ ያድኑናል። ማዳናቸውም የክርስቶስን የማዳን ሥራ የሚተካከል አይደለም፤ እርሱ በሰጣቸው ጸጋ ከእርሱ ዘንድ ይቅርታንና ምሕረትን በማሰጠት የሚያድኑን ናቸው እንጂ።

ቅዱስ ሚካኤል አርምሞንና ትዕግሥትን የሚያስተምረን መልአክ ነው። “የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እንኳን ስለ ሙሴ ሥጋ ከሰይጣን ጋር በተከራከረ ጊዜ የስድብ ቃልን ሊናገር አልደፈረም፤ ‘እግዚአብሔር ይገስጽህ’ አለው እንጂ” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ (ይሁዳ ፩፥፱)

የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤል ጥበቃው አይለየን! ከበዓሉ በረከት ይክፈለን!

ወርኀ ጽጌ

ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ቀን ድረስ ያለው ወቅት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ዘመነ ጽጌ ወይም ወርኀ ጽጌ ተብሎ ይጠራል፡፡ ክረምቱ አልፎ ሰማዩ የሚጠራበት፣ የምድር አበቦች የሚፈኩበትና የሚደምቁበት፣ ሜዳውና ሸንተረሩ ልምላሜ የሚላበሱበት፣ ወንዞች የሚጠሩበትና ለፍጥረታት ሁሉ ተስማሚ አየር የሚነፍስበት ጊዜ ነው፡፡   

ይህ ወቅት ሄሮድስ ከእኔ ሌላ ንጉሥ እስራኤልን ማን ሊገዛ ይችላል? በሚል በይሁዳ ክፍል በቤተ ልሔም በከብቶች ግርግም የተወለደውን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመግደል መነሣቱን የምናስብብት ጊዜ ነው፡፡ የእግዚአብሔር መልአክም በሕልም ለአረጋዊው ዮሴፍ ተገልጦ “ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይሻዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ምድረ ግብጽ ሽሽ፤ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ኑር” በማለት ሲነግረው ሕፃኑና እናቱን ይዞ ሰሎሜን ትረዳቸው ዘንድ አስከትሎ ወደ ግብጽ ሸሸ፡፡

በነቢያት የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ “የይሁዳ ምድር አንቺ ቤተልሔም ከይሁዳ አለቆች ከቶ አታንሺም፤ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ ንጉሥ ከአንቺ ይወጣልና” ተብሎ እንደተጻፈ ሄሮድስ በቅናት ተነሣስቶ በቤተ ልሔምና በአውራጃዎችዋ የተወለዱትን ሁለት ዓመትና ከዚያም በታች ዕድሜ ያላቸውን ፻፵፬ ሺህ ሕፃናትን አስገደለ፤ ዋይታና ጩኸትም ሆነ፡፡ በነቢዩ ኤርምያስ የተነገረው ትንቢትም ተፈጸመ፡፡ “ራሔል ስለ ልጆችዋ ስታለቅስ ብዙ ልቅሶና ዋይታ በራማ ተሰማ፤ መጽናናትንም እንቢ አለች፤ ልጆችዋ የሉምና” (ማቴ. ፪፥፲፰) ተብሎ እንደተጻፈው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችን ፀንሳ በነበረች ጊዜ ለአረጋዊው ዮሴፍ አንዳንድ ጊዜ ቀይ የነበረው መልኳ ተለውጦ እንደ ሮማን አበባ ቀይ፣ ቀይ የነበረው ጸዓዳ ነጭ አበባ፣ ነጭ የነበረው እንደ ጽጌረዳ ቀይ ሲሆንና የሚያውቀው መልኳ ሲለዋወጥበት ዮሴፍ እየደነገጠ እርሷ መሆኗን “ማርያም” እያለ ያረጋግጥ ነበር፡፡ (ነገረ ማርያም) ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ “የበኩር ልጇን እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም” ያለውን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሲተረጉመው “መልኳ እንደ ጽጌረዳና እንደ ሮማን አበባ ይለዋወጥበት ስለነበር በአንድ ዓይነት መልክ አላወቃትም” ብሏል፡፡ (ማቴ. ፩፥፳፭) ያንን ለማውሳት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ያለው ወቅት ወርኀ ጽጌ ተባለ፡፡

የእመቤታችን ወደ ግብፅ ሀገራችን ኢትዮጵያ መሰደድ

ጌታችን ሁለት ዓመት ሲሞላው ሄሮድስ ሊገለው እንደፈለገ የእግዚአብሔር መልአክ ለአረጋዊው ዮሴፍ ከተናገረው በኋላ ወደ ግብፅ ሲሰደዱ በርካታ መከራዎችን አስተናግደዋል፡፡ የቀን ሐሩር፣ የሌሊት ቊር እየተፈራረቁባቸው፣ እሾሁ እየወጋቸው፣ እንቅፋቱ እየመታቸው፣ መውጫና መግቢያው በማይታወቅ በረሃ ውስጥ ብዙ ተሰቃይተዋል፡፡

በግብጽ በረሃ ሲጓዙም እመቤታችን ወደ ትዕማን ቤት በሄደች ጊዜ የቤቱ እመቤት ስታያት “ከየት መጣሽ?” ብላ ጠየቀቻት፤ እመቤታችንም “ከይሁዳ ምድር የተሰደድኩ ስደተኛ ነኝ” አለች፡፡ “አንቺ ሴት ደረቅ ነሽ መሰለኝ፤ በድርቅናሽ ቤትሽን ትተሽ ትዞርያለሽ፤ እንዳንቺ ያለች ቆንጆ ሴት ከአዳራሽ ወደ ዕልፍኝ ይላል እንጂ ሀገሩን ትቶ ሀገር ለሀገር አይንከራተትም” ብላ ተተናኮለቻት፡፡ (ነገረ ማርያም) ዮሴፍም “ለለማኝ ቢኖር ይሰጡታል፤ ባይኖር ደግሞ ካለበት ያድርስህ ይባላል እንጂ እንዲህ እንደ ፍላጻ ልብ የሚወጋ ነገር ምን ያናግርሻል” ብሎ በመለሰላት ጊዜ ኮቲባ የተባለችው የእመቤቲቱ አገልጋይ “ይህ ሽማግሌ ደፍሮ እመቤቴን እንዲህ ይመልስላታል?” ብላ ዮሴፍን በጥፊ ቃጥታ ሕፃኑን ደግሞ ነጥቃ ወደ መሬት ጣለችው፡፡ ሕፃኑም ምርር ብሎ ሲያለቅስ እመቤታችን እርሱን ተከትላ ምርር ብላ አለቀሰች፤ ልታነሣውም በምትሞክርበት ጊዜ ዮሴፍ “ተይው፤ አምላክነቱን ይገለጽ” አላት፡፡ ትዕማንን ከእነ ገረድዋ መሬት ተከፍቶ ዋጣቸው፡፡

ከበረሃውም አልፈው በየዱሩ ከአንዱ መከራ ወደ ሌላው መከራ እየተሸጋገሩ ከቆዩ በኋላ ዕረፍትን ያገኙት ወደ ኢትዮጵያ ከደረሱ በኋላ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች በተዘዋወሩበት ሁሉ ሕዝቡ በእንግድነት እየተቀበለ አስተናግዷቸዋል፤ በዚህም ምክንያት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኢትዮጵያን የአሥራት ሀገር አድርጎ ሰጥቷታል፡፡   

ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ከተፈጸመ በኋላ ጊዜው ሲደርስ ሲያሳድዳቸው የነበረው ሄሮድስ በመሞቱ ለዮሴፍ መልአኩ በሕልም ተገልጦ “የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሙተዋልና ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ” (ማቴ.፪፥፳) አለው፡፡ ዮሴፍም የእግዚአብሔር መልአክ እንደነገረው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንና ልጇን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከሰሎሜ ጋር ይዞ ወደ ገሊላ አውራጃ ሄደ፡፡

አባቶቻችን ይህንን መሠረት አድርገው የእመቤታችንን ስደት በማሰብ በወርኀ ጽጌ በየሳምንቱ ቅዳሜ ለእሑድ ዋዜማ ሌሊት በማሕሌት “አዘክሪ ድንግል ረኀበ ወጽምዐ፣ ድንግል ሆይ ረኀቡንና ጥሙን አሳስቢ” እያልን ከአባቶቻችን ጋር እንዘምራለን፣ ጊዜውንም እናስባለን፡፡ በርካታ ምእመናንም በዚህ ወቅት የእመቤታችንን ስደት በማሰብ ይጾማሉ፣ ይጸልያሉ፡፡

አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ “አዘክሪ ድንግል ንግደቶ ዘምስሌኪ እንዘ ትጐይዪ ምስሌሁ እምሀገር ለሀገር በመዋዕለ ሄሮድስ ርጉም አዘክሪ ድንግል አንብዐ መሪረ ዘውኅዘ እምአዕይንትኪ ወወረደ ዲበ ገጸ ፍቁር ወልድኪ አዘክሪ ድንግል ረኀበ ወጽምዐ ምንዳቤ ወኀዘነ ወኵሎ ዐፀባ ዘበጽሐኪ ምስሌሁ፤ ርጉም ሔሮድስ በነገሠበት ወራት ከአንቺ ጋር ከአንዱ ሀገር ወደ አንዱ ሀገር የተሰደደውን መሰደድ አሳስቢልን፤ በፊትሽና በልጅሽ ፊት የወረደውን መሪር ዕንባ አሳስቢልን፤ ረኀቡን ጥሙን ችግሩንና ኀዘኑን ያገኘሽንም ልዩ ልዩ መከራ አሳስቢልን” (ቅዳሴ ማርያም) ሲል ያዘክራል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በዓለ መስቀል

በመ/ሰላምቀሲስደጀኔሺፈራው (ከአሜሪካ)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመስቀልን በዓል የምታከብረው መስከረም ፲፯ እና መጋቢት ፲ ቀን ነው። እነዚህም አይሁድ በክፋት ቀብረው ሠውረውት የነበረውን መስቀል ለማግኘት ቁፋሮ የተጀመረበት እና መስቀሉ የተገኘበት ዕለታት ናቸው። ክቡር መስቀሉ ከክርስቲያኖች ተሰውሮ የኖረው ለሦስት መቶ ዓመታት ነው።

ክቡር መስቀሉ እንዴት ሊጠፋ ቻለ?

መስከረም ፲፮ እና ፲፯ የሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳር፦ በክፋት የተመሉ አይሁድ፥ በጌታ መስቀል እና መቃብር ምክንያት ይፈጸሙ የነበሩትን አያሌ ተአምራት አይተው በምቀኝነት መነሣሣታቸውን ይተርካል። አይሁድ በኢየሩሳሌምና በአካባቢዋ እስከ ፷፬ ዓ.ም ድረስ ምንም ኃይል አልነበራቸውም። ከ፷፬ ዓ.ም በኋላ ግን ራሳቸውን ከሮማውያን ቅኝ አገዛዝ ነፃ ለማውጣት በጀመሩት ዓመጽ ኢየሩሳሌምን ሙሉ በሙሉ ተቈጣጠሩ። በዚህን ጊዜ ክርስቲያኖቹን ወደ ጌታ መስቀል እና መቃብር እንዳይቀርቡ ከልክለው ቦታውን የቆሻሻ መድፊያ አደረጉት። ከብዙ ጊዜ በኋላ ሥፍራው ትልቅ ጉብታ ሆኖ ከቦታው ጋር ተመሳሳለ። ከዚህም ጋር እስራኤል በየጊዜው ይማርኩ ስለነበር፥ ከምርኮ ሲመለሱም የከተማዪቱ መልክ ስለሚለዋወጥባቸው መስቀሉ የተቀበረበትን ትክክለኛ ጉብታ መለየት አልተቻለም።

በተለይም ከ፻፴፪ – ፻፴፭ ዓ.ም በተደረገው ጦርነት ኢየሩሳሌም ፈጽማ ጠፍታ ነበር። ዳግመኛም ንጉሥ ሐድርያን በ፻፴፭ ዓ.ም. ኢየሩሳሌምን በአዲስ ፕላን በመሥራቱና በጎልጎታ የቬነስን መቅደስ በመገንባቱ ክርስቲያኖቹ ምንም ማድረግ አልተቻላቸውም ነበር። ያን ጊዜ ጎልጎታ ከከተማዋ ውጪ ነበር፥ ዛሬ ግን በአሮጌዋ የኢየሩሳሌም ከተማ ክልል ይገኛል።

መስቀሉ እንዴት ሊገኝ ቻለ?

ክቡር መስቀሉን ፈልጋ ያገኘችው የንጉሥ ቆስጠንጢኖስ እናት ንግሥት ዕሌኒ ናት። ቆስጠንጢኖስ ለክርስቲያኖች ሙሉ ነፃነት የሰጠ ደገኛው የሮም ንጉሥ ነበር። ከዚያ በፊት ምንም ነፃነት አልነበራቸውም።

ቆስጠንጢኖስ ለክርስቲያኖች የሰጣቸው መብት፡-

፩ኛ. ቤተ ክርስቲያንን ከግብር ነፃ አደረጋት።

፪ኛ፦ከመንግሥት ገቢ ለቤተ ክርስቲያን የተወሰነ ድርሻ ሰጣት።
፫ኛ፦ ዕለተ እሑድ የክርስቲያኖች የበዓል ቀን በመሆኗ በግዛቱ ሥራ እንዳይሠራ በ፫፻፳፩ ዓ.ም አወጀ።
፬ኛ፦ ለቤተ ክርስቲያን ኑዛዜ የመቀበልና ውርስ የመውረስ መብት ሰጣት።
፭ኛ በክርስቲያኖች መካከል ለሚፈጠሩ አንዳንድ አለመግባባት፥ ወንጀል ነክ ላልሆነ ጉዳይ ለኤጲስ ቆጳሳት የዳኝነት ሥልጣን ሰጣቸው።

፮ኛ፦ክርስትና የሀገሩ ብሔራዊ ሃይማኖት እንዲሆን አደረገ።

በአጠቃላይ ቤተ ክርስቲያን የወንጌልን የመዳን መልእክት እያወጀች ሐዋርያዊ ጉዞዋን እንድትቀጥል ያደረገ ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ ነው። ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ይህን ያደረገበት ምክንያትም በመስቀል ምልክት የተደረገለት ተአምር ነበር። ይኸውም የሮምን የምዕራቡን ክፍል ይገዛ የነበረው ማክሴንዲዮስ የጦር ኃይሉን ባዘመተበተት ጊዜ፥ እርሱም በበኩሉ «ምታ ነጋሪት፥ ክተት ሠራዊት» ብሎ ለጦርነት ተዘጋጀ። ገና በዝግጅት ላይ እንዳለም፦ «በዚህ ድል ታደርጋለህ፤» የሚል በመስቀል ቅርጽ የተጻፈ ጽሑፍ በጠፈረ ሰማይ አየ። በዚህን ጊዜ፦ ሠራዊቱ በፈረሱ አንገት፥ በጋሻው እምብርት መስቀላዊ ቅርጽ እንዲያደርግ አወጀ።
ሮምን ሙሉ በሙሉ ጠቅልሎ መግዛት የጀመረው ከዚህ በኋላ ነበር። ከዚያ በፊት ለአርባ ዓመታት ለአራት ተከፍላ በኋላም ለሁለት ተከፍላ ትተዳደር ነበር።

ጦርነቱም በመስቀሉ ኃይል ጠላቶቹን ድል አድርጎ ተመለሰ እናቱ ንግሥት ዕሌኒ በልጇ ዘመን የተገኘውን የክርስትና ነፃነት ተጠቅማ በ፫፻፳፯ ዓ.ም. ክቡር መስቀሉን ፍለጋ ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች። በዚያም ጉብታ የሆነውን ሥፍራ ሁሉ በማስቆፈር ብዙ ብትደክምም መስቀሉን ለማግኘት አልቻለችም። በዚህን ጊዜ ኪራኮስ የተባለው አረጋዊ፦ «ደመራ አስደምረሽ፥ ዕጣን አፍስሰሽ፥ ብታቀጣጥዪው ጢሱ ይመራሻል፤» ባላት መሠረት ሳትጠራጠር አደረገችው። የዕጣኑ ጢስ መስቀሉ ከተቀበረበት ጉብታ ላይ እንደ ቀስተ ደመና ተተክሎ በጣት ጠቅሶ የማሳየት ያህል አመለከታት።

ቁፋሮውም መስከረም ፲፯ ተጀምሮ መጋቢት ፲ ተፈጸመ። የተገኙት ሦስት መስቀሎች ስለነበሩ የክርስቶስን መስቀል በተአምራቱ ለዩት። ዕውር አበራ፥ አንካሳ አረታ፥ ለምጽ አነጻ፥ ሙት አስነሣ። ንግሥቲቱም ያን ተአምራትን የሚያደርግ ቅዱስ መስቀል የከበረ ቤተ ክርስቲያን አሠርታ በክብር እንዲቀመጥ አደረገች።

መስቀል፤ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ተላልፎ በመሰጠት ቅዱስ ሥጋውን የቆረሰበት፥ ክቡር ደሙንም ያፈሰሰበት ነውና ሃይማኖታዊ ትርጉም አለው። መሰቀል ድኅነታችን የተፈጸመበት (መዳናችን የተረጋገጠበት) ነው «ኢየሱስም ሆምጣጣውን ከተቀበለ በኋላ ተፈጸመ፥ አለ»ይላል (ዮሐ፲፱፥፴) በመስቀል ላይ የተፈጸመው ድኅነታችን (መዳናችን) ነው። ይኸውም የዕለት ፅንስ ሆኖ በማኅፀነ ድንግል ማርያም የጀመረውን የማዳን ሥራ ነው (ሉቃ. ፩፥፴፩)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ፦ «በእርሱም እንደ ቸርነቱ ብዛት በደሙ ድኅነትን አገኘን፥ ኃጢአታችንም ተሠረየልን» ብሏል። መድኃኒት ከድንግል ማርያም መወለዱን ለእረኞች አስቀድመው የሰበኩት ቅዱሳን መላእክት ናቸው (ሉቃ. ፪፥፲፩) መርገመ ሥጋ መርገም ነፍስን የተወገደበት ቅዱስ መስቀል መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የተወገደበት ነው አዳምና ሔዋንሕገ እግዚአብሔርን በመተላለፋቸው የወደቀባቸው የሥጋና የነፍስ መርገም ለሰው ልጅ በጠቅላላ ተርፎት ነበር። «ነገር ግን በአዳም ኃጢአት ምክንያት ከአዳም እስከ ሙሴ (እስከ ክርስቶስ) የበደሉትንም ያልበደ ሉትንም ሞት ገዛቸው።» ይላል( ሮሜ ፭፥፲፬) ሙሴ ለክርስቶስ ምሳሌ ነው። በኦሪቱ እንደተጻፈው በእንጨት ተሰቅለው የሚሞቱ ርጉማን ነበሩ( ዘዳ.፳፩፥ ፳፫)
ይህንም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፦ «በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው፥ ተብሎ ተጽፎአልና፤ ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ (መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን ያመጣብንን ኃጢአት ለመደምሰስ ተላልፎ በመሠዋት) ከሕግ እርግማን ዋጀን።» በማለት ገልጦታል (ገላ. ፫፥፲፫) ቅዱስ ጴጥሮስም፦ «እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ።» ብሏል (፩ኛ ጴጥ. ፪፥፳፬)

ዲያብሎስ የተሸነፈበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል፤ ዲያብሎስ የተሸነፈበት ነው ጥንተ ጠላታችንን (ገነትን ያህል ርስት፥ እግዚአብሔርን ያህል አባት ያሳጣንን ዲያብሎስን) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድል ያደረገልን በመስቀሉ ነው።«ጥልን በመስቀሉ ገደል፤» ይላልና። (ኤፌ. ፪፥፲፮) ጥል የተባለው ለሰውና ለእግዚአብሔር መጣላት ምክንያት የሆነ ዲያብሎስ ነው። እኛም በኃይለ መስቀሉ ድል እያደረግነው የምንኖር ሆነናል።

የጥል ግድግዳ የፈረሰበት ቅዱስ መስቀል

መሰቀል የጥል ግድግዳ የፈረሰበት ነው፤የጥል ግድግዳ የተባለው ኃጢአት ነው። እርሱም ሰውና እግዚአብሔ ርን ለያይቷቸው ኖሯል። «በደላችሁ በእናንተና በአምላካችሁ መካከል ለይታለች፥ እንዳይሰማም ኃጢአታችሁ ፊቱን ከእናንተ ሠውሮታል።» ይላል (ኢሳ. ፶፱፥፪) ይህ ከእግዚአብሔር ለያይቶን እግዚአብሔርን ሰውሮብን የኖረ የጥል ግድግዳ (በዲያብሎስ ምክር የተሠራ ኃጢአት) የፈረሰው በመስቀል ላይ በተፈጸመ የክርስቶስ ቤዛነት ነው። «በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳ በሥጋው አፈረሰ፤» እንዲል (ኤፌ. ፪፥፲፭)

ዕርቅ የተፈጸመበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል ዕርቅ የተፈጸመበት ፣ሰውና እግዚአብሔር የታረቁት በመስቀል ላይ በተፈጸመ ካሳ ነው። ሰውና እግዚአብሔር በመታረቃቸው ነፍስና ሥጋ፣ሰውና መላእ ክት፣ሕዝብና አሕዛብም ታርቀዋል። እኛ በበደልን እርሱ ክሶ (የደም ካሣ ከፍሎ) ታርቆናል።«ጠላቶቹ ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ታረቅን።» ይላልና (ሮሜ ፭፥፲፤ ፪ኛ ቆሮ. ፭፥፲፰፤ ኤፌ. ፪፥፲፮) በሌላ በኩል ደግሞ «ሁሉንም በእርሱ ይቅር ይለው ዘንድ በመስቀሉ ላይ ባፈሰሰው ደም በምድርና በሰማይ ላሉ ሰላምን አደረገ።» የሚልም አለ (ቈላ. ፩፥፳)
አምላካዊ ይቅርታ የተገኘበት ነው፤ «አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው።» በማለት ገር ፈው የሰቀሉትን በቃሉ ይቅር ብሎአቸዋልና (ሉቃ. ፳፫፥፴፬) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ፦ በሞቱ የሰውን ዘር በጠቅላላው ይቅር እንዳለው ሲናገር፦ «አሁን ግን በፊቱ ለመቆም የተመረጣችሁና ንጹሓን፥ ቅዱሳንም ያደርጋችሁ ዘንድ በሥጋው ሰውነት በሞቱ ይቅር አላችሁ።» ብሏል (ቈላ. ፩፥፳፪)

አምላካዊ ሰላም የተሰጠበት የተገኘበት ቅዱስ መስቀል

ነቢዩ ኢሳይያስ «ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም (ወልድ) ተሰጥቶናልና፥ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል።» በማለት ትንቢት የተናገረለት አምላክ ፍጹም ሰላምን የሰጠን በመስቀሉ ላይ በፈጸመው ቤዛነት ነው። (ኢሳ. ፱፥፯) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም፦ «መጥቶም ቀርበን ለነበርነው ሰላምን፥ ርቃችሁ ለነበራችሁት ለእናንተም ሰላምን ሰጠን።» ብሏል (ኤፌ. ፩፥፲፯)

የእግዚአብሔር ፍቅር የተገለጠበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል የእግዚአብሔር ፍቅር የተገለጠበት ነው። ጌታችን የማታ ተማሪ የነበረውን ኒቆዲሞስን ሲያስተምረው፦ «እግዚአብሔር አንድ ልጁን ቤዛ አድርጎ እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲህ ወዶታልና፤»ብሎታል። (ዮሐ. ፫፥፲፮) ቅዱስ ዮሐንስም በወንጌሉ የጻፈውን የጌታችን ትምህርት መሠረት አድርጎ፦ «በዚህም የእግዚአብሔር ፍቅሩ በእኛ ላይ ታወቀ፥ በእርሱ በሕይወት እንኖር ዘንድ አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና። የእግዚአብሔርም ፍቅሩ ይህ ነው፥ እርሱ ወደደን እንጂ እኛ የወደድነው አይደለንም፥ ኃጢአታችንንም ያስተሠርይልን ዘንድ ልጁን ላከው» ብሏል (፩ኛዮሐ. ፬፥፱-፲፩)

የገነት በር የተከፈተበት ቅዱስ መስቀል

መስቀል የገነት በር የተከፈተበት ነው፡፡ ጌታችን ወደዚህ ዓለም የመጣው፥ ድኅነተ ምእመናንንም በመስቀል ላይ የፈጸመው ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ተዘግታ የነበረችውን ገነትን ለመክፈት ነው። ይህም ይታወቅ ዘንድ፥ በቀኙ ተሰቅሎ፥ «አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ»እያለ ሲማጸነው የነበረውን ወንበዴ፦«እውነት እልሃልሁ፥ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ» ብሎታል(ሉቃ. ፳፫፥፵፪-፵፫)

 የምንመካበት ቅዱስ መስቀል

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፦«ነገር ግን ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት (ዓለም በእኔ ዘንድ ሙት የሆነበት)፥ እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት (እኔም በዓለም ዘንድ ሙት የሆንኩበት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክሕት ከእኔ ይራቅ፤»ብሏል፡፡ (ገላ. ፮፥፲፬)
በመሆኑም ዓለምና ቅዱስ ጳውሎስ በጌታ ደም ላይ በተመሠረተች ቤተ ክርስቲያን እና በደሙ በጸናች ወንጌል ምክንያት ተለያይተዋል። አንዳቸው ለአንዳቸው ሙት ናቸው። ዓለም ሕያው የሆነችልን፥ እኛም ሕያው የሆንላት የሚመስለን የዓለም ፈቃድ ፈጻሚዎች ከቅዱስ ጳውሎስ ልንማር ይገባል። ዓለም ታልፋለች፥ እኛም ከእሷ እንለያለንና።

ከአጋንንት የምንድንበት ቅዱስ መስቀል

በክርስቶስ ቅዱስ መስቀል ከአጋንንት ጦር እንድናለን ቅዱስ ዳዊት በትንቢት፦ «ለሚፈሩህ ምልክትን ሰጠሃቸው፥ ከቀስት ፊት (ከአጋንንት ጦር) ያመልጡ ዘንድ ወዳጆችህም እንዲድኑ።» ያለው ስለ መስቀል ነው። (መዝ. ፶፱፥፬) በመሆኑም በመስቀል ምልክት አማትበን፥ ከአጋንንት ፈተና እንድናለን። መስቀል ኃይላችን ነው መስቀልን በእጅ መጨበጥ፥ በአንገት ማንጠልጠል፥ መሳለም በዓለም ዘንድ ሞኝነት ነው ለእኛ ለክርስቲያኖች ግን ድኅነት የተረጋገጠበት ነው። ለዚህም ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት፥ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና» በማለት ያስተማረን፡፡ (፩ኛቆሮ. ፩፥፲፰)

በመሆኑም በቀራንዮ በመስቀል ላይ አንድ ጊዜ የተገለጠ ኃይለ እግዚአብሔር እስከ ዘለዓለሙ አይለየንም። በመሆኑም ለቅዱስ መስቀሉ እንሰግዳለን። ቅዱስ ዳዊት፦ «እግሮቹ በሚቆሙበት ሥፍራ እንሰግዳለን» ባለው መሠረት የጌታችን እግሮች በመስቀል ላይ፥ ያውም በቀኖት ላይ ስለቆሙ ለመስቀሉ እንሰግዳለን። መስቀሉን በደሙ ቀድሶታልና፥ ለመስቀሉ የሚገባውን ክብር እንሰጣለን። እግዚአብሔር በረድኤት በደብረ ሲና ራስ በቆመ ጊዜ፥ «ወደዚህ አትቅረብ፥ የቆምክባት ሥፍራ የተቀደሰች ናትና፥ ጫማህን ከእግርህ አውጣ፤» በማለት ሙሴን አስተምሮታል፡፡ (ዘዳ. ፫፥፭)

እንኳን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል ይቅርና የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል የቆመበትን መሬት፥ የተቀደሰ በመሆኑ፦«አንተ የቆምክበት ሥፍራ የተቀደሰ ነውና ጫማህን ከእግር አውልቅ» በማለት ኢያሱን ሲያዘው እርሱም የታዘዘውን እንዲደረግ ተረድተናል (ኢያ. ፭፥፲፭)፡፡ እንግዲህ መሬቱን፥ አፈሩን የቀደሰ አምላክ ፦ ሥጋውን የቆረሰበትን፥ ደሙን ያፈሰሰበትን፥ ነፍሱንም አሳልፎ የሰጠበትን መስቀል አልቀደሰውም ለማለት እንዴት ይቻላል? ፈጽሞ አይቻለም።ንግሥት ዕሌኒ በብዙ ድካም ከወርቅ ዙፏኗ ወርዳ ከአፈር ላይ ተቀምጣ፥ ቆፍራ አስቆፍራ መስቀሉን አውጥታለች። ዛሬ በእኛ ዘመን የተቀበረው ዳግም በመስቀሉ ያ የተገኘው ፍቅርና ሰላም ነው።

ፍቅር በጥላቻ፥ ሰላም በጦርነት፥ አንድነት በመለያየት፥ እምነት በክሕደት፥ መንፈሳዊነት በሥጋዊነት የሕዝቦች ውሕደት በዘረኝነት ቆሻሻ ተቀብሮአል። ይህንን ቆፍረን ካወጣን ያን ጊዜ የዘመኑ ዕሌኒዎች እንሆናለን። መስቀሉን ተሸክመን በጥላቻና በዘረኝነት ቆሻሻ የተቀበርንም በቅድሚያ ራሳችንን ቆፍረን እናውጣ፥ ለብዙዎችም እንቅፋት አንሁን። ዘመኑን ከተቀበርንበት የምንወጣበት ያድርግልን።

የእግዚአብሔር ቸርነት፥ የድንግል ማርያም አማላጅነት፥ የመስቀሉ በረከት አይለየን፥ አሜን።

“የቀደመውም አለፈ፤ እነሆ ሁሉም አዲስ ሆነ” (፪ቆሮ. ፭፥፲፰)

እንኳን ከዘመነ ማቴዎስ ወደ ዘመነ ማርቆስ በሰላም አሸጋገረን፡፡

መልካም አዲስ ዓመት!

በኢትዮጵያውያን ዘመን አቆጣጠር የመስከረም ወር የወራት ሁሉ መጀመሪያ ነው፡፡ ይህ ወር ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ ገበሬው በክረምቱ ወራት መሬቱን አልስልሶ፣ ዘሩንም ዘርቶ ምድሪቱም አደራዋን ለመመለስ በልምላሜ የምታጌጥበት ወር ነው፡፡ በዚህም ምክንያት እንስሳት ለምለሙን ሣር ግጠው፣ የጠራውን ውኃ ጠጥተው ረክተው፣ አምረው የሚታዩበት የልምላሜ ወር ነው። ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት “ምድርን ጐበኘሃት አጠጣሃትም፥ ብልጥግናዋንም እጅግ አበዛህ፤ የእግዚአብሔርን ወንዝ ውኃን የተመላ ነው፤ ምግባቸውን አዘጋጀህ እንዲሁ ታሰናዳለህና። ትልምዋን ታረካለህ፥ ቦይዋንም ታስተካክላለህ፤ በነጠብጣብ ታለሰልሳታለህ፥ ቡቃያዋንም ትባርካለህ። በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል። የምድረ በዳ ተራሮች ይረካሉ፥ ኮረብቶችም በደስታ ይታጠቃሉ። ማሰማርያዎች መንጎችን ለበሱ፥ ሸለቆችም በእህል ተሸፈኑ፤ በደስታ ይጮኻሉ ይዘምራሉም” እንዲል። (መዝ. ፷፬፥፱-፲፫)

ቅዱስ ዮሐንስ

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንም ዓመታትን በቸርነቱ ለሚያቀዳጅ ለእግዚአብሔር ምስጋና ለማቅረብ የአዲሱን ዓመት መጀመሪያ ወይም ርእሰ ዐውደ ዓመት “ቅዱስ ዮሐንስ” በሚል ስያሜ ስታከብረው ኖራለች፣ ትኖራለችም። ይህም ሊሆን የቻለበት ምክንያት የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ ሆኖ መገኘቱና የቤተ ክርስቲያን አበው የበዓላትን ድንጋጌ በወሰኑበት ጊዜ የመጥምቁ ዮሐንስ መታሰቢያ በዓል የኢትዮጵያ ርእሰ ዐውደ ዓመት በሚሆን መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር በየዓመቱ የዘመኑ መጀመሪያ በእርሱ ስም እንዲጠራ በመደንገጋቸው ነው። (ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)፡፡  መጽሐፈ ስንክሳር የዓመቱን መጀመሪያ የሆነውን መስከረምን ሲያትት “ይህ የመስከረም ወር የተባረከ ነው፤ እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው” በማለት ያስረዳል። 

የዘመን መለወጫ

ብርሃናት (ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት) የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ይህ ቀን የዘመን መለወጫ ተብሎ ይጠራል። ሌሊቱ ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ቢቆጥሩ ፫፫፷፬ ቀናት ይሆናል፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ ይህን ሲገልጽ “ሌሊቱም ከቀኑ ጋራ ይተካከላል፡፡ ዓመቱም ጠንቅቆ ቢቆጥሩት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ቀን ይሆናል፡፡ (ሄኖ. ፳፮፥፻፬) ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስም አዲሱን ዓመት በተመለከተ ሲገልጽ “ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድስ” (ሰ.ኤር. ፭፥፳፩) በማለት በኃጢአት የወደቅን በንስሓ ተነሥተን፣ የቀማን መልሰን፣ በአዲስ ሰውነትና በአዲስ አስተሳሰብ ከእግዚአብሔር ጋር እርቅ የምንፈጽምበት፣ በሕይወታችንም እንድንለወጥና እንድታደስ ይመክረናል፡፡

ዕንቁጣጣሽ 

ከሁለት አበይት ምክንያት መጠሪያ እንደሆነ ሊቃውንት ይናገራሉ፤ የመጀመሪያው ምክንያት የኖኅ ልጅ ካም ከወንድሞቹ ጋር ምድርን ሲከፋፈሉ በዕጣ አፍሪካ ስትደርሰው መጀመሪያ ያረፈው ኢትዮጵያ ላይ በመስከረም ወር ሲሆን በዚህ ጊዜ የምድሩንና የአበቦቹን ማማር አይቶ ደስ ብሎት ”ዕንቁ ዕጣ ወጣሽል” ሲል ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል። ሁለተኛው ንጉሡ ሰሎሞን ለንግሥት ሳባ “ዕንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንልሽ” ሲል እጅግ በጣም የከበረ ዕንቁ ያበረከተላት በዚህ በመስከረም ወር ስለነበር፤ ከዚህ በመነሣት መስከረም አንድን እንቁጣጣሽ በሚለው ስያሜ እንደሚጠራ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስተምራሉ።  

ዘመን መለወጫ ከላይ ባየናቸው የተለያየ ስያሜ ይጠራ እንጂ ዘመኑ አዲስ እየተባለ ቢጠራም አዲስ መሆን ያለበት ወርና ወቅቱ ብቻ ሳይሆን የእኛ የክርስቲያኖች ሕይወት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ወንድሞቻችን ሰውነታችሁን ለእግዚአብሔር ሕያውና ቅዱስ፣ ደስ የሚያሰኝም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እማልዳችኋለሁ” እያለ በመዋዕለ ሥጋዌው ያስተምር ነበር፡፡ (ሮሜ ፲፪፥፩)

አዲስ ዓመት ሲመጣ ብዙዎቻችን ያለፈውን አንድ ዓመት፣ ከዚያም በፊት የነበረውን የሕይወት ጉዞአችን መመርመራችን አይቀርም፡፡ እግዚአብሔር ሁልጊዜ አዲስ ቀንን እያፈራረቀ ትናንትን አሳልፎ ዛሬን ይሰጠናል፤ ነገር ግን ከትናንት ስህተታችን ለመማርና እግዚአብሔርን ለመፈለግ የምንሻ፣ ወደ ንስሓም የምንመጣ ስንቶቻችን እንሆን? “አሁንም በክርስቶስ የሆነው ሁሉ አዲስ ፍጥረት ነው፤ የቀደመውም አለፈ፤ እነሆ ሁሉም አዲስ ሆነ” (፪ቆሮ. ፭፥፲፰) እንዲል፡፡ አንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን “በቃ በሚቀጥለው ዓመት ንስሓ እገባለሁ፤ ወይም ዛሬን እንደፈለግሁ ሆኜ ነገ ንስሓ እገባለሁ እያለ በቀቢጸ ተስፋ አይኖርም፡፡

እግዚአብሔር አንድ ቀን አይደለም ዓመት ከዚያም በላይ ታግሶ የሚጠብቀን ልጆቹ ስለሆንን ነው፡፡ ስለዚህ ነገ፣ ነገ እያልን በድንግዝግዝ የምንጓዘውን ጉዞ ትተን ዛሬ ንስሓ መግባት ይገባናል፡፡ በአዲስ ዓመትም ያለፈውን በኃጢአት ጨለማ ውስጥ ተዘፍቀን የኖርንበትን ዘመን ለመድገም ሳይሆን በአዲስ ሰውነት፣ በአዲስ ማንነት እንነሣ ዘንድ ንስሓ እንግባ፣ ከእግዚአብሔር ኅብረት እንጨመር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እላችኋለሁ እንዲሁ ንስሓ ስለሚገባ ስለ አንድ ኃጢአተኛ በእግዚአብሔር መላእክት ፊት በሰማያት ደስታ ይሆናል” በማለት እንዳስተማረን ከተኛንበት እንንቃ፣ በኃጢአት፣ በተንኮል፣ በክፋት የቆሸሸውን ሰውነታችን በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን፣ በመልካም ተግባር አንጽተን ወደ ተቀደሰው አዲስ ሰውነት ልንለወጥ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በዓለ ቅዱስ ሩፋኤል

“ሩፋኤል” የሚለው ቃል “ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ” ማለት ነው፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ጳጉሜን ፫ ቀን በዓሉ በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ “ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ” እንዲል (ጦቢ. ፲፪፥፲፭)፡፡  

በሌላ በኩል ደግሞ ሩፋኤል ማለት ከዕብራይስጥ ሁለት ቃላት ተጣምሮ የተገኘ ቃል ነው፡፡ “ሩፋ” ማለት ጤና፣ ፈውስ፣ መድኃኒት” ማለት ሲሆን “ኤል” የሚለው ቃል ደግሞ በሌሎቹም መላእክት ስም ላይ የሚቀጸል ስመ አምላክ ነው:: ይህ መልአክ እንደ ሌሎቹ ሊቃነ መላእክት ሁሉ ያለ ማቋረጥ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔርን ከሚያመሰግኑ ቅዱሳን መላእክት አንዱ ነው፡፡ የሰው ልጆችንም ይጠብቃቸዋል፣ ያማልዳቸዋል፤ ከፈጣሪም ያስታርቃቸዋል፡፡ (ዘካ.፩÷፲፪፤ ዳን.፬÷፲፫፤ ዘፀ.፳፫÷፳፤ መዝ.፺÷፲፩-፲፫፤ ሉቃ..፲፫፥፮-፱፣)፡፡

የቅዱስ ሩፋኤል በዓሉ የሚከበርባቸው ምክንያቶችም አንደኛው በዓለ ሢመቱን ምክንያት በማድረግ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ቅዳሴ ቤቱ ነው፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቍስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ “በበሽታ ሁሉ ላይ በሰው ልጆችም ቍስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው” በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል (ሄኖ. ፲፥፲፫)፡፡ የሰው ልጆችንም በሥጋ ከታመሙበት ደዌም ሆነ ቍስል ይፈውስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ “በሰው ቍስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው” (ሄኖ. ፮፥፫)፡፡

እግዚአብሔር የመካኒቱን ማኅፀን ፈትቶ የተባረከ ልጅን የመስጠትን ጸጋ ለመላእኩ ቅዱስ ሩፋኤል  ሰጥቶታል፡፡ ሴቶች በሚፀንሱበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያቸውም፡፡ የወላድን ማኅፀን እንዲፈታ ስለተሾመ ከጌታ አዋላጅ ብትኖር ባትኖርም ሐኪም ቅዱስ ሩፋኤል አይታጣም፤ በምጥ ጊዜ ሲጨነቁ ሴቶች ሁሉ የመልአኩን መልክ አንግተው ማርያም ማርያም ብለው ማየ ጸሎቱን ጠጥተው ቶሎ ፈጥነው ይወልዳሉ፡፡ ቅድስት ሣራን እና እንትኩይን (የሳሙኤል እናት) ወልዶ ለመሳም ያደረጋቸው ፈታሔ ማኅፀን የሆነው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሕፃኑ (ኗ በማኅፀን እያለ (ች) ተሥዕሎተ መልክዕ (በሥላሴ አርአያ መልኩ /ኳ/ መሳል) ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ ቅዱስ ሩፋኤል በጥበቃው አይለያቸውም፡፡ በመውለጃቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማኅፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀልላቸዋል፡፡

አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን በወለተ ራጉኤል ላይ አድሮ ባሎቿን እየገደለ ቢያሰቃያት ቅዱስ ሩፋኤል ጋኔኑን አስጨንቆ አስወጥቶላታል (ጦቢ. ፫፥፰-፲፯)፡፡ ለቃየን ልጆች ሰይፍና ሾተል መሥራትን፣ የምንዝር ጌጥ ማጌጥን፣ መቀንደብን ያስተማረ አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አስሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው (ሄኖ. ፪፥፲፰)፡፡ “ዳግመኛም እግዚአብሔር ሩፋኤልን፣ አዛዝኤልን እጁን እግሩን አስረህ በጨለማ ውስጥ ጣለው አለው” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሄኖ. ፫፥፭-፯)፡፡ የጦቢትን ልጁ ጦቢያን በሰው አምሳል ተገልጦ ከተራዳው በኋላ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ራሱን ሲገልጥ “የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነትም ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ አላቸው” (ጦቢ. ፲፪፥፲፭)፡፡

በቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት ከተደረጉ ተአምራት መካከል በእስክንድርያ አቅራቢያ በምትገኝ ደሴት በታነጸች ቤተ ክርስቲያኑ ያደረገው ተአምር አንደኛው ነው፡፡ በመጽሐፈ ስንክሳር እና በድርሳነ ሩፋኤል እንደ ተጻፈው ብዙ ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጠች፤ ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና፡፡ የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ዓሣ አንበሪው ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፡፡ ምእመናኑም ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔር በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ፡፡ ያን ጊዜ ቅዱስ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ “እግዚአብሔር አዝዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጥ ጸጥ ብለህ ቁም!” ባለው ጊዜ አንበሪው ጸጥ ብሎ ቆሟል፡፡ በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገልጠዋል፡፡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆኗል፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል ተረዳኢነት ከሁላችን ጋር ይሁንልን፤ አሜን፡፡

ምንጭ፡- መጽሐፍ ቅዱስ፣ መጽሐፈ ስንክሳር፣ ተአምረ ሩፋኤል

ነገረ ጳጕሜን

በመ/ር ተስፋ ማርያም ክንዴ

በዚህም የመጽሐፍ ቃል መሠረት የኢትዮጵያ ሊቃውንት በዓመት ከ፲፪ቱ ወራት የተረፉትን ዕለታት ከወር ባነሱ ዑደቶች በዕለት፣ በኬክሮስ፣ በካልኢት፣ በሳልሲት፣ በራብኢት፣ በሐምሲትና በሳድሲት ሰፍረውና ቀምረው በዓመት ፭ ቀን፣ ከ፲፭ ኬክሮስ፣ ከ፮ ካልኢት አድርገው እነዚህ ዕለቶች ጳጕሜን ፲፫ኛ ወር አድርገውታል።

ኢትዮጵያዊያንና ግብፃዊያን ብቸኛ የባለ ፲፫ ወር መባላቸው ግን ዕለቷ በሌሎች አልኖር ብላ ሳይሆን ሌሎች እንዲሁ በዘፈቀደ ከሌላው ወር ጋር ደርበው ሲያከብሯት ኢትዮጵያና ግብጽ ግን ከላይ ከኬክሮስ እስከ ሳድሲት ባሉት ጥቃቅን የጊዜ መስፈሪያዎች ሰፍረን ቀምረን ስለምናውላት ነው። የዓለም ሀገራትም አንዳንዶቹ ከወራቸው ደርበው የወሩን ቁጥር አንዳንዴ ፴ አንዳንዴ ፴፩ እያደረጉ አሽባጥን (የካቲትን) ደግሞ ለይተው በ፫ቱ ዓመት ፳፰፣ በ፬ኛው ፳፱ እያደረጉ ጳጉሜን ደርበው ያውሏታል። እንደዚህ ከሚያከብሩ ሀገሮች መካከል ሮማዊያን (አፍርንጅ) እና ሶርያ እንዲሁም ይጠቀሳሉ፤ አንዳንዶቹ ደግሞ በ፰ኛው ወር መጨረሻ ስሟን ለዋህቅ ብለው ስለሚያከብሯት ነው።

በሌላ በኩልም ጳጕሜን ማለት ከህፀፅ ጋር ሲሰላ በዓመት የሚገኝ የፀሐይና የጨረቃ ዑደት ትርፍ ማለት ነው። ማክሰኞ ለረቡዕ አጥቢያ ጨረቃ በምሥራቅ በ፬ኛው ኆኅት በ፬ኛው ኬክሮስ ላይ የ፲፭ ዕለት ሙሉ ጨረቃ ሁና ስትፈጠር ፀሐይ ደግሞ በምዕራብ በኩል ልትገባ ፬ ኬክሮስ (፵፰ ደቂቃ) ሲቀራት ተፈጥራ ወዲያው ገብታለች፡፡  “ወይመይጦ ለብርሃን መንገለ መስዕ፤ ብርሃንን ወደ መስዕ(አቅጣጫ) ይለውጠዋል”  እንዳለ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በሰዓታት መጽሐፉ፡፡ ፀሐይ በሰሜን ዙራ በምሥራቅ ስትወጣ ጨረቃ ለመግባት አንድ ኬክሮስ ፶፪ ካልኢት ፴፩ ሳልሲት ፶፰ ራብዒት ፳፯ ሐምሲት ሲቀራት ደርሳባታለች። ራብዒቱንና ሐምሲቱን ደቃቅ ብሎ ትቶ ሌላውን በትናንሽ የብርሃን መስፈሪያዎች እየተጠቀለለ ሲደመር አንድ ኬክሮስ በዓመት ፮ ዕለት ይሆንና ህፀፅን ሲሰጥ ሌላው ደግሞ ጳጕሜን ያስገኛል።

እንዲሁም ጳጕሜን ማለት ከአንድ ዕለት የተገኘ ትርፍ ብርሃን በዓመት ተጠቅሎ ሲሰላ ማለት ነው። ፀሐይ በአንድ ቀን ወጥታ ፭ቱን ኬክሮስ በአንድ ሰዓት ፷ውን ኬክሮስ በ፲፪ ሰዓት አድርሳ ትገባለች፡፡ በቀን ውስጥ ከዚህ የተረፈ ከመውጣቷ በፊትና ከገባች በኋላ መጠኑ ያነሰም ቢሆን ብርሃን አለ፤ ጳጕሜን ማለት ይህ ብርሃን ነው። ይህም ብርሃን በትናንሽ መስፈሪያዎች ሲለካ ከመውጣቷ በፊት ያለው ፳፮ ካልኢት ፲፭ ነሳልሲት ፴ ራብኢት ከገባች በኋላም እንዲሁ ፳፮ ካልኢት ፲፭ ሳልሲት ፴ ራብኢት ሆኖ በድምሩ በቀን ፀሐይ ከመውጣቷና ከገባች በኋላ ያለው የብርሃን መጠን ፶፪ ካልኢት ከ፴ ሳልሲት ከ፷ ራብኢት ወይም ራብኢቱን ወደ ሳልሲት በመቀየር ፶፪ ካልኢት ከ፴፩ ሳልሲት ይሆናል። ይህንንም በአንድ ላይ እየሰበሰብን ስናሰላው በዓመት ፭ ጳጕሜን ይሰጠናል። ፶፪ቱን ካልኢት እስከ አንድ ወር ስንሰበስበው ወይም ስናባዘው ፲፭፻፷ካልኢ ይሆናል፤ እስከ ዓመት ደግሞ ፲፰ ሺህ ፯፻፳ ካልኢት ይሆናል፤ ይህን ወደ ኬክሮስ ለመቀየር በ፷ ሲገድፉት ወይም ለ፷ ሲያካፍሉት። ፫፻፲፪ ኬክሮስ ይሆናል፤ ይህን ወደ ቀን ለመቀየር በ፷ ሲገድፉት ፭ ቀን ከ፲፪ ኬክሮስ ይሆናል፡፡

ይህን ባለበት እናቆየውና ሌላውን እናስላ ፴ውን ሳልሲት እስከ ወር ሲሰበስቡት ፱፻ ሳልሲት ይሆናል፤ እስከ ዓመት ሲሰበስቡት ደግሞ ፲ሺህ፰፻ ሳልሲት ይሆናል፤ ይህን ወደ ካልኢት ለመቀየር በ፷ ሲገድፉት ፻፹ ካልኢት ይሆናል፤ ወደ ኬክሮስ ሲቀይሩት ፫ ኬክሮስ ይሆናል። ይህን ከመጀመሪያው ጋር ስንደምረው ፭ ዕለት ከ፲፭ ኬክሮስ ይሆናል። እንዲሁም ፷ውን ራብኢት ወደ ካልኢት ሲቀይሩት አንድ ሳልሲት ይሆናል፤ ይህን እስከ ወር ቢወስዱት ፴ ይሆናል፣ እስከ ዓመት ቢወስዱት ደግሞ ፫፻፷ ሳልሲት ይሆንና ወደ ካልኢት ሲቀየር ፮ ካልኢት ይሆናል። ሁሉንም በአንድ ላይ እንሰብስበው፡- ከመጀመሪያው ፭ ቀን ከ፲፭ እና ከመጨረሻው ያገኘነው ፮ ካልኢት በዓመት ፭ ዕለት ከ፲፭ ኬክሮስ ከ፮ ካልኢት ያልነው ይህ ነው።

፲፭ቱ ኬክሮስ በ፬ ዓመት ፷ ኬክሮስ ሆኖ አንድ ዕለት ይሆንና በአራተኛው ዓመት በዘመነ ዮሐንስ ጳጒሜን ፮ ዕለት ትሆናለች። ይህችም ዕለት ሰግረ ዮሐንስ ትባላለች፤ ምክንያቱም የዮሐንስን ዓመት የወር መባቻ እያሰገረች ስለምታውል ነው። ፮ቱ ካልኢት ደግሞ እስከ ፮፻ ዓመት ቢሰበሰብ ፴፮፻ ካልኢት ሆኖ በዕለት አንድ ዕለት ይሆንና በ፮፻ ዓመት ጳጒሜን ሰባት ዕለት ትሆናለች፡፡ ይህችም በቁጥር መምህራን ዘንድ እሪና ዕለት ትባላለች። እሪና መንገዱ ብዙ ነው የቀን እሪና አለ፣ የወር እሪና አለ፣ የዓመት ዕሪና አለ። ዓለም የተፈጠረው በዕሪና ነው የሚያልፈው ግን በእሪና ነው የሚሉ አሉ እሱን ግን ወንጌል ዕለቲቱን የሚያውቅ የለም ስለሚል በዚህ ቀን ምጽአት ይሆናል እያሉ ሰውን ከማደናገር የሰው ዕለተ ምጽአቱ ዕለተ ሞቱ ነውና ሁሌም ተዘጋጅተው እንዲጠብቁ ማስተማር የተሻለ ይሆናል።

ከባንዲራዋ ጋር ነጻነቷንና ሉአላዊነቷን የምታሳይበት መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርጋ በራሷ ሊቃውንት እየቀመረች ለዘመናት ይዛው የመጣችው የራሷ የዘመን ቆጠራ ያላት ኢትዮጵያ በራሷ የዘመን ቆጠራ ሃይማኖታዊ ሥርዓቷን ባህሏንና ማንነቷን ስታከናውን ኑራለች፤ ወደፊትም ትኖራለች። ይህን የማያውቁና የማይረዱ አንዳንድ ግለሰቦችና ድርጅቶች ግን ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ኢትዮጵያ ጳጕሜንን እንደ ሌሎች ሀገሮች ከወሯ ደርባ ማክበር አለባት ወይም መተው አለባት ሲሉ መደመጥ ጀምረዋል።

ለመሆኑ ኢትዮጵያ እነሱ እንዳሉት ጳጕሜን ከሌሎች ወራት ደርባ ብታከብር ምን ነገር ይፋለሳል? ብለው ለሚጠይቁ ሰዎች የሚከተሉትን ጥቂት ማሳየዎች እናቀርባለን።

፩ኛ. ቤተ ክርስቲያናችን በጳጕሜን ወር በርካታ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶችን የምታከናውን ሲሆን ከእነዚህም አንዱ ዕለተ ምጽአትን ታከብራለች። መምህራን ጳጕሜን ከክረምት ወደ በጋው የምንሸጋገርባት ናት፡፡ ክረምት ደግሞ ከላይ ዝናብ ከታች ጎርፍ ነጎድጓድ መብረቅ ወዘተ የሚበዛበት ነውና የዚህ ዓለም ምሳሌ፣ በጋው ደግሞ ክረምቱ የሚያልፍበት ብርሃን የሚወጣበት አዝመራው የሚያፈራበት ነው ብለው ከምጽአት በኋላ በምንወርሰው መንግሥተ ሰማያት ይመስሉና በዚህ ወር ዕለተ ምጽአትን እንድናስብ አድርገውናል። እኛ ክርስቲያኖች ደግሞ ዕለተ ምጽአትን በዚች ወር ብቻ ሳይሆን ዘወትር እሱን እያሰብን ክፉ ከመሥራት እንድንጠበቅ መጽሐፍ ያስተምረናል፡፡ (ማቴ. ፳፬ እና ፳፭) ስለዚህ ጳጉሜን ወር አታክብሩ ማለት ሃይማኖታችሁን፣ ባህላችሁን፣ ታሪካችሁን ተዉ እንደማለት ይቆጠራል፤ ሰው ደግሞ ይህን ማንነት ትቶ እንደ እንሰሳት ሊኖር አግባብ አይደለም።

፪ኛ. በዚህ ወር ከመልአኩ ሩፋኤል በዓል በተጨማሪ በቤተ ክርስቲያን ተሰባስበን ርኅዎ ሰማይን (የሰማይ መከፈት) እናከብራለን። ርኅዎ ሰማይ ጳጕሜን ሦስት ይከበርና ከዚያ ማግስት ያለውን ቀን አንድ ብሎ ቆጥሮ በየ ፶፪ ቀኑ በዓመት ሰባት ጊዜ ይከበራል። ርኅዎ ሰማይ ማለት የሰማይ መከፈት ማለት ነው። በሰማይ መከፈትና መዘጋት ኑሮበት ሳይሆን ጸሎት የሚያርግበት ያልታየ ምሥጢር የሚታይበት እንደሆነ በ(ማቴ. ፫፥፩) ላይ ተጽፎ እናገኘዋለን። ከዚህ በተጨማሪ በጳጕሜን ወር ብዙ ምእመናን በመጾም ጸበል በመጠመቅ ከመንግሥት ሥራ ጀምሮ በነጻ መንፈሳዊና ሥጋዊ ትሩፋቶችን በማከናወን አዲሱን ዓመት ለመቀበል የሚዘጋጁባት ዕለት ናት።

፫ኛ. የጨረቃ ወርኃዊ ልደትና የወቅቶች መፋለስ፡- ጨረቃ የራሷ የቀን፣ የ፲፭ ቀን የወርና የዓመት ዑደት አላት፡፡ ለማሳያ ያህል የያዝነውን ዓመት የ፳፬፲፯ ዓ.ም የዓመት ዑደቷን የምትጨርሰው በፀሐይ ነሐሴ ፲፰ ቀን ነው። ይህ ማለት የመስከረም ጨረቃ ነሐሴ ፲፱ ቀን ትወለዳለች ከነሐሴ ፲፪ ከጳጕሜ ፭ ስናመጣ ፲፯ ይሆናል፡፡ የመስከረም ወር ጨረቃ የምትቆየው ፳፱ ዕለት ስለሆነ ይህን ለመሙላት ከመስከረም ፲፪ እናመጣና በሚቀጥለው ቀን የጥቅምት ጨረቃ ትወለዳለች፤ ስለዚህ ጳጕሜን የለችም ማለት ግን የመስከረም ወር ጨረቃ መስከረም ፲፪ ቀን መጨረሷን ትታ ወደ ፲፯ ትሄዳለች ማለት ነው። ይህ ደግሞ መምህራን ከሠሩት የጨረቃ የወር መንገድና የዓመት መንገድ ጋር የተፋለሰ ይሆናል። አራቱን ወቅቶችንም ብናይ እንደዚሁ መፋለስ ይፈጥራል፡፡ አንድ ቀን ስንል የራሱን ኬንትሮስ ከኬንትሮሱ ጋር የራሱን ፊደል ከፊደሉ ጋር የራሱን የፀሐይ ኆኅት እንዲሁም በመራሒ ወተመራሒ ሕግ የራሱን የቀን የወር የ፲፪ ወርና የዓመት ከዋክብትን ይዞ የሚጓዝ ነው እንጂ እንደፈለገ አንዱን ዕለት ከአንዱ የምንጨምረው አይደለም፡፡ በጥቅሉ በቁጥር መምህራን ዘንድ አንዱን ዕለት እንደፈለግን ከአንደኛው ዕለት ጋር ደርበን እናውል ማለት አንዱን እጅ ከአንዱ እጅ አንዱን እግር ከአንዱ እግር ጋር እንጨምር እንደማለት እንደሚቆጠር ልብ ማለት ይገባል። ሲጠቃለል ኢትዮጵያ የራሷ ባህል ታሪክ ሃይማኖት ያላት ይህንም በትውፊትና በመጽሐፍ ቅዱስ ይዛ የቆየች ሀገር ናት ስለዚህ አንድ ሰው ውሸት ቢናገርና በውሸታሞች መካከል ቢደገፍ ሌሎችም ውሸት ይናገሩ እንደማይባል ኢትዮጵያም ሌሎች በንጉሣቸው በጣኦታቸው ስም በየጊዜው እየቀያየሩ የዘመን ቆጠራን ቢያከብሩ የራሷን እውነት ትታ የእነሱን ውሸት ትቀበል እንደማይባል መረዳት ያስፈልጋል።

ስብሐት ለእግዚአብሔር

በዓለ ደብረ ታቦር!

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐሥሩን ደቀ መዛሙርት በእግረ ደብር ትቶ ሦስቱን የምስጢር ደቀ መዛሙርት የተባሉትን ቅዱስ ጴጥሮስን፣ ቅዱስ ዮሐንስንና ቅዱስ ማርቅዱስን ይዞ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ የወጣበትና በዚያም ከመቃብር ሊቀ ነቢያት ሙሴን፣ ከብሔረ ሕያዋን ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን አምጥቶ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ዕለት በማሰብ ነሐሴ ፲፫ ቀን በየዓመቱ በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

ደብረ ታቦር ከዘጠኙ ዐበይት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓላት አንዱ ሲሆን በዓሉም በምእመናን ዘንድ ቡሄ በመባል ይታወቃል፡፡ በዓለ ደብረ ታቦር ለምን ቡሄ ተባለ? ቡሄ ማለት ‘መላጣ፣ ገላጣ’ ማለት ነው፡፡ ታቦር ተራራ ከገሊላ ባሕር በምዕራባዊ ደቡብ በኵል ዐሥር ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከናዝሬት ከተማ በስተ ምሥራቅ፣ ከዮርዳኖስ ወንዝ በስተ ምዕራብ አቅጣጫ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእስራኤል በርካታ ታላላቅ ተራሮች እያሉ ለምን ደብረ ታቦርን መረጠ? ብለን መጠየቃችን አይቀርም፡፡   

ምሥጢረ መንግሥቱን ለምን በታቦር ተራራ ላይ ገለጸ?

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ሌሎች ተራሮች እያሉ ደብረ ታቦር ላይ ክብሩን የገለጠው ስለ ሁለት ምክንያት ነው፡፡ እነርሱም፡- ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ ትንቢቱን ለመፈጸም ማለታችን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፣ ስምህንም ያመሰግናሉ” እያለ እንደዘመረው (መዝ. ፹፰፥፲፪) ይህን ትንቢትንም ለመፈጸም በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ክብረ መንግሥቱን ገለጠ፡፡

ሁለተኛው ደግሞ ምሳሌውን ለመፈጸም ጌታችን በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ተገለጠ፡፡ ቀድሞ ባርቅና ሠራዊቱ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ ወጥተው ሲሳራን ድል አድርገውበታልና (መሳ. ፬፥፮) ጌታም በልበ ሐዋርያት ጥርጥርን እና ፍቅረ ሢመትን (የሥልጣን ፍቅር) ያሳደረ ሰይጣንን ድል ነስቶላቸዋል፡፡ ከዚህም በመነሣት የደብረ ታቦር በዓል “የደቀ መዛሙርት (የተማሪዎች በዓል)” ተብሎም ይጠራል፡፡

እስራኤላውያን በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ሥራ በመሥራታቸው በአሶር በነገሠው በከነዓን ንጉሥ በኢያቡስ እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፤ የሠራዊቱም አለቃ ሲሣራ ነበር፡፡ ዘጠኝ መቶ የብረት ሰረገሎች ነበሩትና የእስራኤልንም ልጆች ሃያ ዓመት አስጨነቃቸው፡፡ (መሳ. ፬፥፩-፫) በዚያም ወራት የለፊዶት ሚስት ነቢይቱ ዲቦራም እስራኤልን ትገዛቸው ነበር፡፡ ባርቅን ጠርታ “ሄደህ ወደ ታቦር ተራራ ውጣ፣ ከአንተም ጋር ከንፍታሌምና ከዛብሎን ልጆች ዐሥር ሽህ ሰዎች ውሰድ፤ እኔም የኢያቢንን ሠራዊት አለቃ ሲሣራን፣ ሰረገሎቹንም፣ ሕዝቡንም ሁሉ ወደ አንተ ወደ ቂሶን ወንዝ እሰበስባለሁ፤ በእጄም አሳልፌ እሰጥሃለሁ” አለችው፡፡ ዲቦራም ከደባርቅ ጋር ወደ ቃዴስ ሄደች፡፡ ሲሣራም ባርቅ ከሠራዊቱ ጋር ወደ ደብረ ተራራ እንደ ወጣ ሰማ፡፡ ባርቅ ሠራዊቱን ይዞ ከደብረ ታቦር ተራራ በወረደ ጊዜ ሲሣራና ሠራዊቱን አስደነገጣቸው፡፡ ሲሣራም ከሰረገላው ወርዶ በእግሩ ሸሸ፡፡ ባርቅም ሲሣራንና ሠራዊትን ድል ነስቶበታል፡፡ (መሳ. ፬፥፩-፲፯)

ሦስቱን ሐዋርያት ብቻ ይዞ ለምን ወደ ደበረ ታቦር ተራራ ወጣ?

፩. ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊሊጶስ ቂሳርያ ደቀ መዛሙርቱን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?” ብሎ ጠየቃቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ!” ብሎ መሰከረ፡፡ (ማቴ. ፲፮፥፲፮) ቅዱስ ጴጥሮስ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት የመሰከረውን ምስክርነት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ይሰሙ ዘንድ፣ ከነቢያት (ሙሴና ኤልያስ) አንደበት ይረዱ፣ በተዓምራት የደነደነ ልባቸውን ይከፍት ዘንድ የጌታችንን ነገረ ተዋሕዶ ከመሰከረ ከስድስት ቀን በኋላ አዕማድ ሐዋርያት ተብለው የተጠሩትን ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ያዕቆብና ቅዱስ ዮሐንስን ይዞ ወደ ተራራ አወጣቸው (ማቴ. ፲፯፥፩-፲)፡፡

፪. ሙሴን ከመቃብር፣ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን ለምን አመጣቸው?

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከሕግ (ከኦሪት)፣ ነቢዩ ኤልያስ ደግሞ ከታላላቅ ነቢያት የተመረጡበት ሌላው ምክንያት እግዚአብሔር በዘመነ ኦሪት ከሙሴ ጋር ቃል በቃል በደመና በሚነጋገርበት ጊዜ ሙሴ “ፊትህን (ክብርህን) አሳየኝ” ብሎ እግዚአብሔርን በጠየቀው ጊዜ “ሰው አይቶኝ አይድንምና ፊቴን ማየት አይቻልህም“ ብሎታል፡፡ በዚህም ብቻ ሳያበቃ “እስከ አልፍም ድረስ እጄን በላይህ እጋርዳለሁ፤ በዚያ ጊዜ ጀርባዬን ታያለህ፤ ፊቴን ግን ለአንተ አታይም” ብሎታል፡፡ (ዘፀ.፴፫፥፲፫-፳፫)

በፊልጶስ ቂሳርያ ጌታ ሐዋርያትን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደሆነ ይሉታል?” ብሎ ለጠየቃቸው ጥያቄ ሲመልሱ “ሙሴ ነው ይሉሃል ፤ እንዲሁም የኃይል ሥራህን ተመልክተው ኤልያስ ነው ይሉሃል” ብለው ነበር፤ ሙሴን ከመቃብር፤ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ “አንተ በኋለኛው ዘመን ምስክር ትሆነኛለህ” ብሎት ነበርና ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ “የኤልያስን ጌታ ኤልያስ ነው ይልሃል? እግዚአ ኤልያስ፤ አምላከ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ” ሲል በደብረ ታቦር ተገኘ፡፡ ታያለህ የተባለው ሙሴም አየ፣ ትመሰክራለህ የተባለው ኤልያስም መሰከረ፡፡

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ “ጌታ ሆይ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው” ሲል ተደምጧል፡፡ ቃል በቃል ስናየው ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታ ሆይ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ማለቱ “አንተ እያበላኸን እየፈወስከን፣ ሙሴ እነዚህ መከራ ያደርሱቡኛል ይገድሉኛል ያልካቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያን እንዳይመጡ በደመና እየጋረደ፣ ቢመጡም አልያስ እሳት እያዘነመ እያባረራቸው በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ሲሆን ምሥጢራዊው መልእክቱ ግን “የኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት በሚታመንበት፣ ወልድ ዋሕድ በምትለው ሃይማኖት መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ ሰይጣን ድል በተደረገባት በታቦር ተራራ ምሳሌም በምትሆን በወንጌል ሕይወት፣ በቤተ ክርስቲያን መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ነው፡፡

ወቅቱ በሀገራችን የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ብርሃን የሚገለጥበት፣ ወገግታ የሚታይበት፤ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚሸጋገርበት ወቅት በመሆኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት እንዲሉ፡፡ እንዲሁም በዓለ ደብረ ታቦር ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት፤ ብርሃን የታየበትና ድምፀ መለኮቱ የተሰማበት ዕለት ስለሆነ ‘የብርሃን’ ወይም ‘የቡሄ’ በዓል ይባላል፡፡

በዚህ ሰሞን ልጆች የተገመደ ገመድ አዘጋጅተው ማጮሃቸው ሁለት ዓይነት ምስጢር የያዘ ትውፊታዊ ተግባር ነው፡፡ የመጀመሪያው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ግርፋቱንና ሞቱን እናስብበታለን፡፡ ሁለተኛው ደግሞ፤ ጅራፍ ሲጮህ እንደሚያስደነግጥ ሁሉ ከጌታ ጋር የነበሩት ሦስቱ ደቀ መዛሙርትም አብ በደመና ሆኖ ሲናገር መደንገጣቸውንና መውደቃቸውን የሚያስታውስ ነው፡፡ ድምፁን ስንሰማ የባሕርይ አባቱን የአብን ምስክርነት ቃል፤ እንደ ነጎድጓድ ድምፅ ያስታውሰናል፡፡

እናቶችም ለዚህ በዓል የሚሆን ዳቦ ለመጋገር ስንዴያቸውን ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉ ይሰነብታሉ፡፡ በበዓሉ ዋዜማ (ነሐሴ ፲፪ ቀን) ሕፃናት በየቤቱ እየዞሩ ቡሄ በሉ፤ ቡሄ መጣ፤ ያ መላጣ፤ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ … እያሉ ይጫወታሉ፡፡ በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ እያነሡ ይሰጧቸዋል፡፡ ለምን ሙልሙ ዳቦ ተዘጋጅቶ ለልጆች ይሰጣቸዋል ስንል፡- ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዕለት እረኞች ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል፡፡ ‘ቡሄ’ ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና በበዓሉ ችቦ የሚበራውም ከዚህ ታሪክ በመነሣት ነው፡፡

ጌታችን በፊታቸው ተለወጠ፤ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ

ሦስቱ ሐዋርያትና ሁለቱ ነቢያቱ በተራራው ሳሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሲጸልይ ሳለ መልኩ በፊታቸው ተለወጠ፡፡ ፊቱም እንደ ፀሐይ ብሩህ ሆነ፡፡ ልብሱም እንደ በረድ ጸዓዳ ሆነ፡፡ ጌታችን “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ” እንዳለ የሕይወት ብርሃን፣ የሰው ልጆች ተስፋ የሆነውን ብርሃኑን ገለጠ፡፡ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብትንም ብርሃን ያለበሰ እርሱ ነው፡፡ ለመላእክት፣ ለጻድቃን ለቅዱሳን ሁሉ የጽድቅ ብርሃንን ያደለ የማይጠፋ ብርሃን እርሱ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ተራራ ብርሃነ መለኮቱን ገለጠ፡፡ ይህ ሁሉ ነገረ ተዋሕዶን እንዲረዱ የተደረገ መገለጥ ነው፡፡ ሰውነቱን አልካዱም፣ አምላክነቱን ግን ተጠራጥረው ነበርና አምላክነቱን ገለጠላቸው፡፡  

ቅዱስ ጴጥሮስም የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የፊቱ ብሩህ መሆን፣ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ መሆን እንደዚሁም የቅዱሳን የነቢያት መምጣት እና ከጌታችን ጋር መነጋገራቸውን ከሰማ በኋላ “እግዚኦ እግዚእ ሠናይ ለነ ኃልዎ ዝየ፤ ጌታ ሆይ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው“ አለ፡፡ ቅዱሳን ነቢያቱ የወትሮ ሥራቸውን እየሠሩ ማለትም ሙሴ ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላት እያስገደለ፤ ኤልያስም ሰማይ እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናመ እያቆመ፤ አንተም አምላካዊ የማዳን ሥራን እየሠራህ ገቢረ ተአምራትህን እያሳየህ፤ በዚህ በተቀደሰ ቦታ በደብረ ታቦር መኖር ለእኛ እጅግ መልካም ነው” አለ፡፡ አምላካዊ ፈቃድህስ ከሆነ በዚህ ተራራ ላይ አንድ ለአንተ፤ አንድ ለሙሴ፤ አንድ ለኤልያስ ሦስት ዳስ እንሥራ ብሎም ጠየቀ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ “በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” ሲል ጌታችን በተአምራቱ ሲራቡ እያበላቸው፣ ሲጠሙ እያጠጣቸው፣ ሲታመሙ እየፈወሳቸው፣ ቢሞቱ እያነሣቸው፤ ሙሴም እንደ ቀድሞው ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላትን እየገደለ፤ ኤልያስ ደግሞ ሰማይን እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናም እያቆመ በደብረ ታቦር ለመኖር መሻቱን ያመለክታል፡፡ ዳግመኛም “ሦስት ጎጆ እንሥራ፤ አንዱን ለአንተ፤ አንዱን ለሙሴ፤ አንዱን ለኤልያስ” በማለት የእርሱንና የሁለቱን ሐዋርያት ጎጆ ሳይጠቅስ አርቆ መናገሩ በአንድ በኩል ነቢያቱን አስቀድሞ ባልንጀሮቹ ሐዋርያትን አለመጥቀሱ ትሕትናው ትሕትናውን፤ እንደዚሁም ከጌታችን ጋር ለመኖር ያለውን ተስፋ ያመለክታል፡፡  

የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ሲናገር ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፡፡ በደመናም “ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ፤ ልመለክበት የወደድኩት ለምስጢረ ተዋሕዶ የመረጥኩት የምወደው፣ የምወልደው ልጄ ይህ ነው እርሱንም ስሙት” የሚል ቃል መጣ፡፡ በዚህም የሥላሴ ምስጢር ለዓለም ተገለጸ፡፡ እግዚአብሔር አብ በደመና ሆኖ “የምወደው የምወልደው ልጄ ይህ ነው” እያለ፣ እግዚአብሔር ወልድ ሥጋን ተዋሕዶ ፍጹም አምላክ ሲሆን ፍጹም ሰውም ሆኖ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በነጭ ደመና ተመስሎ ተገልጸዋል፡፡ ስለዚህም ደብረ ታቦር ጌታችን ብርሃነ መለኮቱ፣ ክብረ መንግሥቱ የገለጠበት እንዲሁም የሥላሴ አንድነትን ሦስትነት የተገለጠበት ነው ብላ ቤተ ክርስቲያናችን ታስተምራለች፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መምህር አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ .ም፣ ገጽ ፫፻፲፭፫፻፲፯፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ ፳፻፯ .ም፣ ገጽ ፻፲፩፡፡       

ክረምትና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ለመደበኛው ትምህርት ራሳቸውን በማዘጋጀት በውጤት ታጅበው ለሚቀጥለው ዓመት ለመሸጋገር አቅማቸውን ሁሉ ተጠቅመው ጊዜአቸውን ሰጥተው ሲተገብሩ ማየት የተለመደ ነው፡፡ “የሚተክልም የሚያጠጣም አንድ ናቸው፤ ሁሉም እንደ ድካማቸው ዋጋቸውን ይቀበላሉ” (፩ኛ ቆሮ. ፫፥፰) ተብሎ እንደተጻፈው ድካሙ ብዙ ነው፡፡ ነገር ግን በራስ ጥረት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔርም ፈቃድና ድጋፍ እንደሚያስፈልግ መረዳት ይገባል፡፡ “እኔ የወይን ግንድ ነኝ፤ ቅርንጫፎቹም እናንተ ናችሁ፤ በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ ብዙ ፍሬ የሚያፈራ እርሱ ነው፤ ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና፡፡” (ዮሐ. ፲፭፥፭) በማለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደነገረን ከእርሱ ጋር መሆን ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔርን የሚፈልግ ልብ በፍሬ ይታጀባልና፡፡

በወጣትነት ለሥጋዊው ሕይወት መውጣት መውረድ እንደለ ሆኖ ለመንፈሳዊው ሕይወትም ጊዜ መስጠት፣ በጸሎት መትጋት፣ በንስሓ መመላለስ፣ ከበጎ ነገር ጋር መተባበር ከአንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን የሚጠበቅ ጉዳይ ነው፡፡ ሥጋን ብቻ ለማስደሰት በመሮጥ መንፈሳዊ ምግብ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል ብንዘነጋ ምን እናተርፋለን? ስለዚህ ወጣቶች (የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች) ለመንፈሳዊ ሕይወታችው ከፍተኛ ትኩረት ሊሰጡና በመንገዱም ሊመላለሱ ይገባል፡፡

በወጣትነት ዘመን ስሜታዊነት የሚንጸባረቅበት ጊዜ ነው፡፡ ይህን ጊዜ በጥበብና በማስተዋል ማለፍ ካልተቻለ ለተለያዩ ክፉ ሥራዎች (ሱሶች፣ እግዚአብሔርን መርሳት፣ በጎ ነገርን አለማድረግ፣ …) መጋለጥን ያስከትላል፡፡ በተለይም እግዚአብሔርን አለማሰብ እንደ ቃሉም አለመመላስ በቀሪው ሕይወታቸው የሚያሳድረው ተጽእኖ ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን ዐስብ” (መክ. ፲፪፥፩) አንዲል በወጣትነት ፈጣሪን መፈለግ ይገባል፡፡ ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን ከሕፃንነት ጀምሮ በሰንበት ት/ቤት እንዲታቀፉ፣ የእግዚአብሔርንም ቃል እየተማሩ እንዲያድጉ የምታደርገው፡፡  

ማኅበረ ቅዱሳንም አገልግሎቱን በግቢ ጉባኤት ላይ በማተኮር ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ላይ በመሥራት የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል፡፡ ለተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው በተጓዳኝ መንፈሳዊ ትምህርትን በማስተማር፣ ሕይወታቸውን እንዲፈትሹ፣ ውጤታማም ሆነው እንዲወጡና በኦርቶዶክሳዊ እምነታቸው እንዲጸኑ ከፍተኛ ጥረት ያደርጋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችም የቀሰሙትን መንፈሳዊ ዕውቀትና ሕይወት ወደ ተግባር ለመለወጥ የሚረዳቸው ጊዜ ቢኖር በክረምቱ ወራት ትምህርት ተዘግቶ ወደ ቤተሰቦቻቸው ለዕረፍት ሲሄዱ ነው፡፡ በዚህ ወቅት የዕረፍት ጊዜያቸውን በአግባቡ ሊጠቀሙበት ይገባል፡፡ ዕረፍት ላይ መሆናቸው ሊያዘናጋቸው ስለሚችል አገልግሎቱ ላይ በማተኮር ራሳቸውን እንዲጠብቁ በአጥቢያቸው በሚገኝ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ በመሳተፍ እንደተሰጣቸውም ጸጋ ማገልገል፣ ዕውቀታቸውን ማካፈል፣ ለሌችም አርአያ መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡  

ሌላው በክረምት ወቅት የግቢ ጉባኤት ተማሪዎች ሊያደርጉት የሚገባው በተለያዩ በጎ አድራጎት ሥራዎች ላይ በመሳተፍ በተሰጣቸው ዕውቀት፣ ገንዘብና ጉልበት የተቸገሩትን በመደገፍ ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ዕረፍት ላይ መሆናቸው በርካታ በጎ ሥራዎችን ለመሥራት ዕድሉን ይፈጥርላቸዋል፡፡ “ለሥራ ከመትጋት አትስነፉ፤ በመንፈስ ሕያዋን ሁኑ፤ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ ለጸሎት ትጉ፡፡ በችግራቸው ቅዱሳንን ለመርዳት ተባበሩ፤ እንግዳ መቀበልንም አዘውትሩ” (ሮሜ. ፲፪፥፲፩-፲፬) በማለት እንደተነገረና ክረምቱ ምቹ ጊዜ በመሆኑ መትጋት ይገባል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሌላው በክረምት ወቅት ሊያደረጉት የሚገባቸው ነገር ቢኖር ለአብነት ትምህርት ትኩረት ሰጥተው ይማሩ ዘንድ ነው፡፡ አንዳንድ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የመደበኛ ትምህርቴን በደንብ እንዳልከታተል እንቅፋት ይሆንብኛል እያሉ በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠውን የአብነት ትምህርት ከመማር ችላ የሚሉ አሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ግን  ጊዜን መድቦ በዕቅድ ራስን ካለመምራት ጋር የሚመነጭ በመሆኑ ሲሸሹ ይታያሉ፡፡  ነገር ግን አጠገባቸው ያሉት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ጊዜአቸውን በአግባቡ በመጠቀም የአብነት ትምህርትን በመማር ለክህነት ሲበቁ እንመለከታለን፡፡ ስለዚህ በመንፈሳዊው ሕይወት ራስን ለማሳደግና በጎደለው ቦታ በመሙላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል በአጥቢያቸው በሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ወይም አቅራቢያቸው ባለ አብነት ትምህርት ቤት ገብተው መንፈሳዊውን ትምህርት መማር ይጠበቅባቸዋል፡፡

የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በክረምቱ ሰፊ ጊዜ ስለሚኖራቸው ሳይዘናጉ ከሌሎች በጎ አድራጎት ሥራዎችና አገልግሎት በተጓዳኝ ለሚቀጥለው ዓመት ትምህርታቸው የሚያግዟቸውን መጻሕፍት በመመርመር ለአዲሱ ዓመት ትምህርት ራሳቸውን ማዘጋጀትም ይገባቸዋል፤ ካለ ንባብ የሚያሳልፉት ቀን ሊኖር አይገባምና፡፡

በአጠቃላይ በክረምት የዕረፍት ወቅት እንደመሆኑ በመዝናናትና በስንፍና በመመላለስ የገነቡትን መንፈሳዊ ሕይወት ችላ እንዳይሉ ጥንቃቄ በማድረግ ባላቸው ጊዜ ራሳቸውንና ሌሎችን በመርዳት ከበረከቱ እንዲሳተፉ ያስፈልጋል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር