ቃና ዘገሊላ

እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በጥምቀት በዓል ማግስት ጥር ፲፪ ቀን የቃና ዘገሊላ በዓል ይከበራል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃና ዘገሊላ በተደረገ ሠርግ ቤት ያደረገውን ተአምር በማሰብ በዓልን ታደርጋለች፡፡ በዓሉ ቃና ዘገሊላ የሚል ስያሜ ያገኘው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ክፍል ቃና በተባለችው ቦታ በፈፀመው ተአምር መነሻነት ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃና በዶኪማስ ቤተ በተደረገ ሠርግ እመቤታችን ለሠርገኞቹ ዘመድ ነበረችና ከእናቱ ከድንግል ማርያም እንዲሁም መምህርን ጠርቶ ደቀ መዛሙርቱን መተው ሥርዓት ስላልሆነ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ተገኝቷል፡፡ በሠርጉ ቤትም ሥርዓቱ እየተከናወነ ሳለ የተዘጋጀው የወይን ጠጅ አለቀባቸው፡፡ ይህን የተገነዘቡት ዶኪማስና አስተናባሪዎቹ ተደናግጠው ሳለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የወይን ጠጁ ማለቁን ተረድታ ጭንቀታቸውን ወደሚያቀልለው ልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ዘንድ ቀርባ “ልጄ የወይን ጠጅ አልቆባቸዋል” አለችው፡፡ እርሱም መልሶ አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም አላት፡፡ ይህም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የሚውልበትና ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለሰው ልጆች ሁሉ ለዘለዓለም ድኅነት ያድል ዘንድ ጊዜው አለመድረሱን ሲያመለክት ነው፡፡ እመቤታችንም ለአገልጋዮቹ የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ አለቻቸው፡፡ በቦታው የነበሩትን ስድስት ጋኖች ውኃ ሞልተው እንዲያመጡ አዘዘቻቸው፡፡ እያንዳንዱም ጋን ሁለት ወይም ሦስት እንስራ ይይዙ ነበር፡፡ አስተናባሪዎቹም ውኃውን በጋኖቹ ሞልተው አቀረቡለት፣ ውኃውንም ወደ ወይን ለወጠው፡፡  እነርሱም እየቀዱ ለታዳሚዎች አቀረቡ፡፡

ታዳሚዎቹም በወይን ጠጁ ልዩ ጣዕም ተደንቀው ሙሽራውን ጠርተው ሰው ሁሉ መልካሙን የወይን ጠጅ አስቀድሞ ያጠጣል፤ ከጠገቡ በኋላም ተርታውንም ያመጣል፤ አንተ ግን መልካሙን የወይን ጠጅ እስከአሁን አቆየህ አሉት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም በቃና ዘገሊላ ያደረገው የተአምራት መጀመሪያ ይህ ነው፤ ክብሩንም ገለጠ፤ ደቀ መዛሙርትም አመኑበት፡፡ (ዮሐ.፪፥፩፲፩)

የቃና ዘገሊላ ጥንተ ነገሩ ወይም ታሪኩ የተፈፀመው በሌላ ጊዜ ቢሆንም አባቶቻችን የውኃን በዓል ከውኃ በዓል ጋር ለማክበር ብለው ወደ ጥር ፲፪ አምጥተውታል፡፡ ይህም ውኃ ወደ ወይን የተለወጠበትን በዓል ከጌታ ጥምቀት በዓል ጋር ለማስተሣሠር በማሰብ ነው፡፡ በመሆኑም የቃና ዘገሊላ በዓል ጥር ፲፪ ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሣይነግሯት በልብ ያለውን የምታውቅ እናት ናትና የሠርጉ አስተናባሪዎች ይህ ጎደለ ሳይሏት የልቡናቸውን ሐዘን ተመልክታ ከልጇ ከወዳጇ አማልዳ የጎደላቸውን ሞልታለች፤ ያስጨነቃቸውንም አርቃለች፤ ለችግራቸውም ደርሳላቸዋለች፡፡ ሳይነግሯት የልቡናን አይታ ካማለደች ስሟን ጠርተው ለሚለምኗት ሁሉ እመቤታችን ትደርሳለችና ዘወትር ወደ እርሷ እንጸልይ ዘንድ ይገባል፡፡   

ከእናታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ረድኤት በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን!

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *