“ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት አርአያ የሚሆን ትውልድን በመቅረጽ የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል”

አቶ አበበ በዳዳ

 (በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ኃላፊ)

ክፍል ሁለት

በእንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ድረ ገጽ አዘጋጅ ከአቶ አበበ በዳዳ የማስተባበሪያው ኃላፊ ጋር ያደረገውን ክፍል አንድ ቆይታ ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በነበራቸው ቆይታም የግቢ ጉባኤት አገልግሎት ማስተባበሪያ ዋና ዋና ተግባራት፣ ከማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች ከማእከላት እና ከግቢጉባኤያት ጋር በቅንጅት የሚከናወኑ ተግባራት፣ እንዲሁም የሚያጋጥሙ ችግሮችና መፍትሄዎቻቸውን በተመለከተ የሰጡትን ምላሽ ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በክፍል ሁለት ያደረግነውን ቆይታ ደግሞ ቀጥለን እናቀርባለን፡-

አሁን ጎልቶ ከሚታየው የዓለም አቀፋዊነትና የዘመናዊነት አስተሳሰብ አንጻር ግቢ ጉባኤያት   ተማሪዎች ሕይወት ከመታደግ አንጻር ምን እየተሠራ ነው?

አቶ አበበ፡- ወጣትነትን በአግባቡ ካልመሩት የሚጎዳንና የሚጠቅመንን ሳንለይ አዲስ ነገር ለመሞከር የምንፈጥንበት የዕድሜ ክልል ነው፡፡ በተለይም በዚህ ዘመን ወጣቶችን እየፈተነ ያለው የዓለም አቀፋዊነትና የዘመናዊነት አስተሳሰብ ለበርካታ ችግሮች ተጋላጭ ሲያደርጋቸው እንመለከታለን፡፡ የግቢ ጉባኤት አገልግሎት ማስተባበሪያም ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት  የሚገቡ ተማሪዎችን በማሰባሰብ ይህንን የወጣትነትና ሁሉን ልሞክር ባይነት ዘመናቸውን በመግራት እግዚአብሔርን በመፍራት እንዲኖሩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ይገኛል፡፡

ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገቡ ወጣቶች ከቤተሰብ የመራቅ ዕድላቸው ከፍተኛ ስለሆነ ጥንቃቄን ይሻልና በአንድ ላይ ለማግኘት አመቺ ከመሆኑ አንጻር ማኅበረ ቅዱሳን ኃላፊነት ወስዶ ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ፣ የመማሪያ መጻሕፍትን አዘጋጅቶ ተከታታይ ትምህርት ይሰጣል፡፡ መንፈሳዊነትን የሕይወታቸው አካል አድርገውም ከክፉ ሁሉ ርቀው እጇን ዘርግታ ለጥፋት ከምትቀበላቸው ዓለም ተለይተው ያገለግሉ ዘንድ ትኩረት ተደርጎ ይሠራል፡፡

በሙያቸውም ዕውቀትንና ክህሎትን ይዘው በተሠማሩበት ሁሉ በታማኝነትና በቅንነት እንዲያገለግሉ አቅጣጫ ማሳየት ነው የእኛ ሥራ፡፡ በዚህም መሠረት የዓለም አቀፋዊነትንና የዘመናዊነትን አስተሳሰብ በመንፈሳዊ ሚዛን መዝነው ሕይወታቸውን እንዲመሩ መንፈሳዊውን ትጥቅ በማስታጠቅ ለአገልግሎት እናሠማራለን፡፡

በተጨማሪም ሥልጠናዎች ይሰጣሉ፣ የምክክር መርሐ ግብራት ይደረጋሉ። እነዚህ ደግሞ በጣም ብዙ ልምድ እና ዕውቀት እንዲገበዩ ይረዷቸዋል፡፡ ሌላው የአንድነት ጉባኤያት፣ የጽዋ ማኅበር፣ የጉዞ እና የንስሓ አባት መርሐ ግብራት ይዘጋጃሉ፤ ይህም ተማሪዎቻችን ራሳቸውን እንዲገዙ፣ ዓለምን የመረዳት ግንዛቤአቸው ከፍ እንዲል ያደርጋቸዋል፡፡ በድረ ገጽ፣ በመጽሔት፣ … በመሳሰሉት የሚዲያ አማራጮችም መረጃዎችን የመሥጠቱ ሥራ ይሠራል፡፡

በምረቃ ሰሞን ግን ብዙ ጊዜ ተመራቂ ተማሪዎች ፶፣ ፻ ቀናት እያሉ ሥጋዊ ሥራዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ለመዝናናት ትኩረት ስለሚሰጡ ለኃጢአት ራሳቸውን አሳልፈው ሲሰጡ እንመለከታለን፡፡ ይህንን ለመከላከል በየጉባኤያቱ የተለያዩ ይዘት ያላቸውን መንፈሳዊ መርሐ ግብራትን በማዘጋጀት ከግቢ ሲወጡ በሕይወታቸው ሊገጥማቸው ከሚችሉ ነገሮች እንዲጠበቁ የምክር አገልግሎት እንዲያገኙ ተማሪዎችን የመታደግ ሥራዎች ይከናወናሉ።

ማኅበረ ቅዱሳን ላለፉት ፩ ዓመታት በርካታ የግቢ ጉባኤት ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡ ነገር ግን ከምረቃ በኋላ አገልግሎት ላይ  ሲሳተፉ አይታይምና ይህንን ችግር ለመፍታት ምን እየተደረገ ነው?

አቶ አበበ፡- ይህንን ጥያቄ ብዙዎች ሲጠይቁ እንሠማለን፡፡ ነገር ግን የአገልግሎት ብያኔያችንን ማስተካከል ይኖርብናል፡፡ አገልግሎት ማለት የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ብቻ አይደለም፡፡   ያስመረቅናቸውን ተማሪዎች ሁሉም ቢመጡ እዚህ መያዝ እንችላለን ወይ? የሚለው ነገር ግልጽ መሆን አለበት፡፡ የምናስተምራቸው ተማሪዎች ለሀገር፣ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለማኅበረሰብና ለራሳቸው የሚጠቅሙ ሥራዎችን እየሠሩ ይገኛሉ፡፡ በአገልግሎትም በተሰማሩበት ቦታ ሁሉ  በዋናው ማእከል፣ በማእከል፣ በወረዳ ማእከል፣ በግንኙነት ጣቢያ፣ በሰ/ት/ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ ታቅፈው ያገለግላሉ፡፡

አገልግሎትን ስናስብ ማኅበረ ቅዱሳን  ሕንጻ ላይ ብቻ የምናየው ከሆነ ልክ አይደለም፡፡ በግቢ ጉባኤ ያስተማርናቸው በሰ/ት/ቤት የሚያስተምሩ፣ የአብነት ትምህርት የሚያስተምሩ እና ሥልጠና የሚሰጡ ናቸው። አገልግሎትን ጠቅለል አድርገን ካላየነው በስተቀር ሰው ራሱንና ቤተሰቡን  በትክክል መምራት ከቻለ መጨረሻ ላይ እንዲሆኑ የሚፈለገው የጽድቅ ሥራ እንዲሠሩ እና እንዲጸድቁ ነው ፡፡

የመንግሥት መዋቅር ውስጥ ገብተው በታማኝነት እያገለገሉ ያሉ የግቢ ጉባኤ ፍሬዎች ብዙ ናቸው፡፡ ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ያስተማራቸው ተማሪዎች የት ናቸው? ብሎ መጠየቅ አይገባም፤ ፊት ለፊት የምናየው ተጨባጭ እውነት አበረታች ነውና፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የበለጠ አንድነታችንን ለማጠናከር እየተሠሩ ያሉ አበረታች ሥራዎችም አሉ፡፡ አንዱ “ዓለም አቀፍ የግቢ ጉባኤያት ምሩቃን ሕብረት” በሁለት ወር አንድ ጊዜ ጉባኤ እየተሠራ ሁሉም ማእከላት በቀኑ እያሰቡ እንዲያገለግሉ ይደረጋል፤ በ ኢኮኖሚ ለማስተሳሰር ሙከራ እና ጥረት ይደረጋል፣ ነጻ የትምህርት ዕድል እንዲያገኙ የጋራ ማኅበራዊ ትስስር እንዲኖራቸው ይደረጋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከተመረቁ በኋላ ለሥራ በተሠማሩበት ቦታ ቅድስት ቤት ክርስቲያንን እና ሀገርን በታማኘት በቅንነት እንዲያገለግሉ ምን ይመክራሉ?

አቶ አበበ፡- እግዚአብሔር ወደ ምድር ሲያመጣን በዓላማ ነው እና ዓላማን ማወቅ ተቀዳሚው ነገር ነው፡፡ ተማሪዎች በግቢ ጉባኤ ቆይታቸው መንፈሳዊውን ትምህርት እንዲማሩ ዕድሉን የሰጣቸው እግዚአብሔር መሆኑን ማሰብ አለባቸው፡፡ ወደ  ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሲገቡ መንፈሳዊው ማዕድ ተዘጋጅቶ ነው የሚጠብቃቸውና ይህንን ዕድል ሊጠቀሙበት ይገባል፡፡

የመጡት መንግሥት በመደባቸው ትምህርት ዘርፍ ተመረቀው እንዲወጡ ቢሆንም እግዚአብሔር ፈቃዱ ሆኖም መንፈሳዊ ትምህርት ጎን ለጎን አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ስለዚህ የተሰጣቸውን መክሊት በአግባቡ መጠቀም ያስፈልጋል። አንድ ተመራቂ ከራሱ ሕይወት ነው መጀመር ያለበት፤  ኦርቶዶሳዊ ሲሆን ለሰው ሁሉ ክብር ይኖረዋል፣ እኩል ለሰው ሁሉ ይራራል ፣ ክፉ ነገር ሁሉ ያንገበግበዋል፡፡ ስለዚህ ዋናው ኦርቶዶሳዊ ሆኖ ለራሱ፣ ለቤተሰቡ፣ ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር መኖር ይገባዋል።

ሁለተኛ በእያንዳንዱ በሚሠማራበት ቦታና የሥራ መስክ የቤተ ክርስቲያን አምባሳደር ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አምባሳደር ደግሞ የክርስቶስን መስቀል ተሸክሞ ነው የሚኖረው፡፡ ያንን የተሸከመው መስቀል የክርስቶስን መከራና ሥቃይ፣ ለሰው ልጆች ሁሉ የከፈለውን ዋጋ በማሰብ በአባቶች ቡራኬ በአደራ መስቀል እናስመርቃቸዋለን፡፡ ምንድነው ማድረግ ያለብኝ፣ እውነት የተሰጠኝን አደራ በአግባቡ እየተወጣሁ ነው? በምሠራበት፣ በምኖርበት አካባቢ እንደ ኦርቶዶክሳዊ የሚጠበቅብኝን ነገር እየተገበርኩ ነው ወይ? እያለ ማሰብ መቻል አለበት እንጂ በሌሎች ተጸእኖ ውስጥ መውደቅ የለበትም፡፡

ሌሎች እርሱ ያደረገውን መልካምነት እንዲከተሉ እንጂ ሌሎች የሚያደርጉትን ጥፋት በመከተል መጓዝ የለበትም፡፡ ለሁሉም የሰው ልጆች እኩል የሚያገልግል፣ እኩል በፍትህ የሚመራ ከሆነና በሙያው ያለ አድልዎ መስጠት የሚችለውን አገልግሎት መስጠት ከቻለ ለሌላው አርአያነቱ የጎላ ነው፡፡ ይህንንም መሠረት አድረጎ ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት አርአያ የሚሆን ትውልድን በመቅረጽ የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል፡፡

ለሰጡን ማብራሪያ እያመሰገን የመጨረሻ መልእክትዎን ቢያስተላልፉ?

አቶ አበበ፡- የግቢ ጉባኤ አገልግሎት የታወቀ አገልግሎት ነው፡፡ ታሪክን ወደ ኋላ ስንመለከት እግዚአብሔር ባወቀ በእግዚአብሔር ፈቃድ የተመሠረተ ነው፡፡ በተለይ ከፍተኛ ተቋማት ውስጥ ያለው ወጣት የሰው ኃይል እንዳይባክን በአግባቡ ቁም ነገር ላይ እንዲወል እግዚአብሔር ያዘጋጀልን አንዱ መድረክ ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን መድረክ በአግባቡ ለሚቀጥለው ጊዜ ማሻገር ያሰፈልጋል፡፡ ይህን አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ደግሞ የተለያዩ አካላት ድርሻ አላቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል በዋነኛነት የተማሪ ቤተሰቦች ትልቁን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡

ልጆቻቸው ወደ ከፍተኛ ተቋማት  ሲገቡ ጎን ለጎን በግቢ ጉባኤ አገልግሎት ውስጥ መሳተፍ እንዳለባቸው በደንብ ትኩረት ሰጥተው በማስገንዘብ ሊልኳቸው ይገባል፡፡ መንፈሳዊውን ትምህርት ቢማሩ መንፈሳዊ ሕይወታቸው ጠንካራ ይሆናል፣ ከአልባሌ ቦታ ይርቃሉ፣ ዓላማም ይኖራቸዋል፡፡ አሁን አሁን እየተቸገርንበት ያለውን የዘረኝነትና የብሔር አመለካከትን በማራቅ የሰው ልጅ አንድ የእግዚአብሔር ፍጡር መሆኑን የሚረዳ አስተሳሰብ እንዲኖረው ያግዘዋል፡፡

ቤተሰብ ልጆቻቸውን በሰ/ት/ቤት እንዲሳተፉ እንደሚያደርጉ ሁሉ ወደ ከፍተኛ ተቋማት ሲመጡ ደግሞ ግቢ ጉባኤ እንዲሳተፉ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ስ/ት/ትቤት የሚማሩት እንደተጠበቀ ሆኖ ይህንንም እየተማሩ በአገልግሎት ክፍሎች እየተሳተፉ የድርሻቸውን መወጣት ይገባቸዋል፡፡

ሌላው ማን ነው የሚያስተምረን? የሚለውን ማወቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡  ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ስኖዶስ ፈቃድ ዕውቅና ያለውና በመላው ዓለም በመንፈሳዊ አገልግሎት የሚሳተፍ ማኅበር መሆኑን መረዳት፣ እንርሱንም ኃላፊነትም ወስዶ በግቢ ጉባኤያት መንፈሳዊ ትምህርቱን እያስተማራቸው እንደሆነ ሊረዱ ይገባልል፡፡

ሌላው ሰ/ት/ቤቶች፣ ማኅበራት፣ የአካባቢ ምእመናን፣  የቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች ይህ ኃላፊነት በጋራ የተሰጠን ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን መምሀር መድቦ ካስተባበረ አጥቢያው የሚገኘው ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ቦታ በማመቻችት በጋራ አገልግሎታችንን በተቀናጀ ሁኔታ እንድናገለግል ጥሪ አስተላፋፍለሁ፡፡ ምክንያቱም እንደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸው የመማር መብት አላቸውና ይህንን ትብብር እንዲያደርጉ፣ በመንግሥት መዋቅር ሥር ያሉ አካላትም የግቢ ጉባኤ አገልግሎት ማለት ለሀገር ሰላም፣ ለመቻቻል፣ አብሮ ለመኖር ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነውና የበኩላቸውን ድርሻ በመወጣት የዘረኝነት እና የጎሰኝነት አስተሳሰብን ማስወገድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ እንደ ሀገር አንድ ሆኖ ለመኖር የሚያግዝ አገልግሎት ስለሆነ ይህን መረዳትም ያስፈልጋል፡፡

ግቢ ጉባኤ ማለት በሥነ ምግባር የታነጹ፣ በሥራቸው ደግሞ አንቱ የሚባሉ ሰዎች የሚወጡበት ነው። መልካም ትዳር፣ መልካም ቤተሰብ መመሥረት የሚቻለው በሃይማኖት በምግባር የቀና ትውልድ መፍጠር ሲቻል ነው፡፡ በተለያዩ ጊዜያት ከጋብቻ ይልቅ ፍቺ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ስለመምጣቱ በቅርቡ የአዲስ አባባ ከተማ ያወጣው ሪፖርት ያመለክታል፡፡  እንደዚህ ዓይነቱን ማኅበራዊ ቀውስ ከማስወገድ አንጻር ወጣቶችን ከመጀመሪያው ጀምሮ በሥነ ምግባር የታነጹ ሆነው ለትዳራቸው፣ ለቤተሰቦቻቸው፣ ለልጆቻቸው ክብር እንዲሰጡ አደርጎ ማብቃት አሰፈላጊ ነው፡፡  እንዲህ የሚያደርጉ ተቋማትን ደግሞ መንከባከብ ያስፈልጋል። ለዚህ የተለየ ድጋፍ ባይደረግ እንኳን በአገልግሎቱ ላይ እንቅፋት እንዳይፈጥሩ መልእከቴን አስተላልፋለሁ፡

በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

አቶ አበበ፡- እኔም አመሰግናለሁ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *