ኒቆዲሞስ

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ዘለዓለም ሥላሴ

ኒቆዲሞስ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስን እንዳስተማረው

እንኳን ለዐቢይ ጾም ሰባተኛ ሳምንት (ኒቆዲሞስ) አደረሳችሁ/አደረሰን።

ክብር ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር መጥቶ በመዋዕለ ሥጋዌው በኪደተ እግር ከቦታ ቦታ እየተመላለሰ የምስራቹን ቃል ሲያውጅ እስራኤላውያን የተቀበሉት በተደበላለቀ ስሜት ነበር። በአንድ በኩል ሕዝቡ ለብዙ ዘመናት በባርነት ሲገዛ ስለነበር ከሮማውያን ቅኝ ግዛት ነጻ የሚያወጣቸው መሲህ ይፈልጋሉ እና ነጻ አውጭ የሚፈልጉበት ነበር። በሌላ በኩል ደግሞ ሕዝቡ ለብዙ ዘመናት በባርነት ቀንበር ስለደከመ ተስፋ በመቁረጥ ተዳክሞ ነበር። መሲህ ቢመጣ እንኳ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት ጦር ይዞ ሰራዊት አስከትሎ ነው ብለው ያምኑ ነበር። ስለዚህም ነበር ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መሲህ ነኝ ብሎ ሲመጣ ለመቀበል ፈቃደኞች ያልነበሩት። ለዚህም ማሳያ ይሆነን ዘንድ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከዐቢይ ጾም አንዱን ሳምንት አድርጋ በሰባተኛው ሳምንት እንደምታከብረው በዕለቱ በሚነበበው የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል ፫÷፩-፲፪ እንደተገለጸው ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስ ለተባለ የአይሁድ አለቃ ያስተማረው ትምህርት እንዲሁም የኒቆዲሞስ ጥያቄና ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረው ትምህርት ይገልጽልናል።

ኒቆዲሞስ የሚለው ቃል የግሪክ ቃል ሲኾን ኒኮስ ድል፣ ደሞስ ሕዝብ ነው። ትርጓሜውም ድል ማድረግ ወይም አሸናፊነት(victory of the people or conqueror of the people) ማለት ነው። ከእስራኤላዊ ወገን የሆነ እስከ መጨረሻው ከተከተሉት አንዱ የሆነው ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ እና ከአይሁድ አለቆችና መምህራና አንዱ ነው። በዚያን ጊዜ የአይሁድ አለቆች ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ምልክት አሳየንእያሉ ይፈታተኑት በነበረበት ወቅት ጌታችን ስለ ሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ ቢያስተምራቸውም እነርሱ ባልገባቸው ጊዜ የእጆቹን ተአምራት የታመሙትን ሲፈውስ እየተመለከቱ ልባቸውን ከማቅናት አምላክነቱን ከማመን ይልቅ የኦሪት ሕጋችንን ሻረ በማለት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ጊዜ ከአይሁድ አለቆች አንዱ የሆነው (ዮሐ. ፫÷፩)፣ ፈሪሳዊው (ዮሐ. ፫÷፩)፣ መምህረ እስራኤል የሆነው(ዮሐ. ፫÷፲)፣ ምሁረ ኦሪት (ዮሐ. ፯÷፶፩) የሆነው ኒቆዲሞስ ግን እንደ ባልንጀሮቹ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሳይቃወም በሌሊት ወደ እርሱ ዘንድ እየሔደ ወንጌልን ይማር ነበር። ጌታችን ኢየሱስም በነፍስ የታመሙትን በቃሉ፣ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ ኒቆዲሞስ ሰምቶና ተመልክቶ በመምህርነቱ ሳይታበይ፤ አለቅነቱን፣ ባለጸጋነቱን፣ እና ሥልጣኑን መመኪያ ሳያደርግ፤ በልቡናው የተሣለውን እውነትን ማግኘት ፈለገ፤ ከጌታውና ከመምህሩ ከክርስቶስ ዘንድ በሌሊት ይገሰግስም ነበር። (ዮሐ. ፫፥፩) ምስክርነቱን እንዲህ ሲል መስጠትም ጀመረ፦ “መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን። እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና።” (ዮሐ.፱፥፳፬፤ ሐዋ.፲፥፴፰)።

ስለምን በሌሊት መጣ ቢሉ

፩. ለእምነት ከመምጣቱ አስቀድሞ በሌሊት መጣ የሚለውን ለማጠየቅ

፪. በኋላ ጌታውን ለመገነዝ የሚመጣ ነውና ለግንዘት ከመምጣቱ አስቀድሞ ወደ ጌታ መጣ ሲል ነው (ዮሐ. ፲፱፥፴፱-፵)።

፫. በመዓልት ከሚመጡ ሰዎች አስቀድሞ በሌሊት መምጣቱን ለማጠየቅ ነው።

፬. የቀን ልቡና የማይሰበሰብ ባካና ነው ኅሊና ይሰረቃል፤ የሌሊት ልቡና ደግሞ የተሰበሰበ እና ክ ነው፤ ትምህርቱን ለመረዳት በቀን ሳይሆን በሌሊት መምጣቱን ልቡናውን ለጌታ መስጠቱን ለማጠየቅ ነው።
፭. ከንቱ ውዳሴን ሽቶ ማለትም አንተ የአይሁድ አለቃ ስትሆን እንዴት ትማራለህ እንዳይባል ሰው በማይመጣበት ከሰው ተለይቶ ሊማር ሽቶ በሌሊት መጣ።
፮. ምሁረ ኦሪት ነውና ምሥጢር ሊያደላድል ነው። በቀን ጌታን አምስት ገበያ ሕዝብ ይከተለው ስለነበር ለመጠየቅ አልተመቸውም ነበር። ጌታም በአእምሮ ያልጎለመሱ ሰዎችን ያስተምር ነበርና በምሳሌ እየመሰለ ያስተምራቸው ነበር። ቅዱስ ጳውሎስ “እኔም፥ ወንድሞች ሆይ፥ የሥጋ እንደ መሆናችሁ፥ በክርስቶስም ሕፃናት እንደ መሆናችሁ እንጂ መንፈሳውያን እንደ መሆናችሁ ልናገራችሁ አልቻልሁም። ገና ጽኑ መብል ለመብላት አትችሉም ነበርና ወተት ጋትኋችሁ፤ ገና ሥጋውያን ናችሁና እስከ አሁን ድረስ ገና አትችሉም። ቅናትና ክርክር ስለሚገኝባችሁ ሥጋውያን መሆናችሁ አይደላችሁምን? እንደ ሰው ልማድስ አትመላለሱምን?” እንዲል አጥንት ለመቆርጠም አልደረሱም ነበር (፩ኛቆሮ. ፫፥፩-፫)።

ኢትዮጵያዊው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ  በጾመ ድጓው እንደገለጸው “ኒቆዲሞስ ስሙ ዘሖረ ኀቤሁ ቀዲሙ ሌሊተ ወይቤሎ በጽሚት ረቢ ነአምን ብከ ከመ እምኀበ አብ መጻእከ ሖረ ኀቤሁ ዘስሙ ኒቆዲሞስ ወይቤሎ ለኢየሱስ ረቢ ሊቅ ንሕነ ነአምን ብከ ከመ እምኀበ አብ መጻእከ ከመ ትኩን መምህረ ወበምጽአትከ አብራህከ ለነ ወሰላመ ጸጎከነ አንሥእ ኃይለከ ወነዓ አድኅነነ፤ አስቀድሞ በሌሊት ወደርሱ ይሔድ የነበረ ስሙ ኒቆዲሞስ የሚባል ሰው በቀስታ “ሊቅ ሆይ ከአብ ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን” አለው። ኒቆዲሞስም ወደ እርሱ ሔደ፤ ረቢ ኢየሱስንም ሊቅ (አዋቂ) እንደሆንክ ለማስተማር ከአብ ዘንድም እንደመጣህ እኛ እናውቃለን፤ በምጽአትህም አበራህልን፤ ሰላምንም ሰጠኸን፤ ኃይልህን አንሳ፤ መጥተህም አድነን አለው።” ብሎ እንደገለጸልን ይህ ኒቆዲሞስ በትጋት  ከመምህሩ ከአምላኩ እንዴት እንደተማረ እና የተማረውንም እንዴት በተግባር እንደገለጽ ያስረዳናል። ይሄንንም በማድረጉ በመትጋቱ ኒቆዲሞስ በሌሊት ወደ ጌታው በመገስገሱ ከእግሩ ስር ቁጭ ብሎ በመማሩ “ለምሥጢረ ጥምቀት መገለጥ ምክንያት ሆነ (ዮሐ ፫÷፩-፳፩) ኒቆዲሞስ ገና ምሥጢሩ ስላልገባው “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኀፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” በማለት ለጌታ ጥያቄ አቅርቧል (ዮሐ. ፫፥፮፤ ፩ኛ ጴጥ. ፩፥፳፫) “እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም። ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፤ ከመንፈስ የተወለደ መንፈስ ነውና” (ኤፌ. ፭፥፳፮) ብሎ ጌታችን ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ ቢያስረዳውም ያኔ ገና ምሥጢሩ ሊገለጥለት ግን አልቻለም ነበር። “ይህ እንደምን ይቻላል?” በማለትም ጌታን ጠይቋል በኋላ ግን በመጠኑ ሲገባው  “አዋቂ ነን የሚሉትን አሳፈራቸው” (ዮሐ ፯÷፶፩) “ፈሪሳዊያንን ሕጋችን አስቀድሞ ሳይሰማ የሠራውንም ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን” ብሎ አይሁድን ተከራክሮ አሳፍሯቸዋል ወደ ፍጹምነት ደረጃ ሲደርስ ደግሞ “በሌሊት ይማር የነበረ በግልጽ ጌታን ለመገነዝ በቃ” (ዮሐ ፲፱÷፴፰) “ጌታችን በቀራንዮ አደባባይ ራሱን ለዓለሙ ቤዛ አድርጎ ሲሰጥ በዋለበት እየዋሉ በአደረበት እያደሩ ትምህርቱን ሲማሩ የነበሩ እስከ ሞት ከአንተ አንለይህም ያሉት ደቀ መዛሙርቱ ከዮሐንስ በስተቀር ሁሉም ሲበታተኑ በዘጠኝ ሰዓት ቀራንዮ የነበረ ኒቆዲሞስ ነበር። ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ሆኖ የክርስቶስን ሥጋ ከጲላጦስ ለምኖ የገነዘ፣ የክርስቶስን ክቡር ሥጋ ከርቤና የእሬት ቅልቅል ያርከፈከፈለት ወደ ሐዲስ መቃብር ያወረደውም ኒቆዲሞስ ነበር”። ይህም “ወአልቦ ፍርኃት ውስተ ተፋቅሮትነ ፍጹም [ፍቅር ፍርኃትን አውጥቶ ይጥላል]” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፳፯፥፶፰፤ ፩ኛ ዮሐ. ፬፥፲፰) የኒቆዲሞስን ፍጹም ለጌታችን ያለውን ፍቅር ያሳየናል።

ኒቆዲሞስ ለብዙ ነገሮች አርአያ የምናደረገው ሲሆን ለአብነትም ያክል የሚከተለውን እናስታውስ፦

፩. ትግሃ ሌሊት (በሌሊት መትጋት) – ኒቆዲሞስ ቀን እየሠራ በሌሊት ወደ ጌታ በመሄድ ለትጋት አብነት ሁኖናል።  ኒቆዲሞስ ወደ ጌታው ለመማር የሄደው በእኩለ ሌሊት ነበር። ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ስለ ጽድቅህ ፍርድ በእኩለ ሌሊት አመሰኝህ ዘንድ እነሣለሁ ይላል። (መዝ. ፻፲፰፥፷፪) ኒቆዲሞስ በሚታሰብበት የዐቢይ ጾም ሰንበት በጸሎተ ቅዳሴ የሚዜመው የክቡር ዳዊት መዝሙር ፦ “ሐወፅከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ፤ አመከርከኒ ወኢተረክበ ዐመፃ በላዕሌየ፤ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ ዕጓለ እመሕያው [በሌሊት ጎበኘኸኝ፤ ልቤንም ፈተንኸው፣ ፈተንኸኝ፣ ዐመፅም አልተገኘብኝም፣ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር]” (መዝ.፲፮ ÷ ፫—፬) ይህን የሚያስረዳ ነው። ሊቁ ማር ይስሐቅ “ሌሊት ጌታን ለማመስገን የተፈጠረ ድንቅ ጊዜ ነው” እንዳለ ራስን በቀንም በሌሊት ከሚመጣ ፈተና መጠበቅ ይገባል።  ቅዱስ ይስሐቅ ሶርያዊ “ከመኝታህ በፊት የምታደርገውን ጸሎት ትተህ እንድትተኛ መንፈስህ ሲገፋፋህ እሺ ብለህ አትቀበለው። እንዲያውም መዝሙረ ዳዊትን ጨምርና ሌሊቱን በሙሉ ስትጸልይ እደር” ይላል። ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊትም “በሌሊት በቤተ መቅደስ ውስጥ እጆቻችሁን አንሡ፥ እግዚአብሔርንም ባርኩ እንዳለ”( መዝ ፻፴፬÷፩)። ሌሊት በባሕርይው ኅሊናን ለመሰብሰብ በተመስጦ ለመማር የሚመች ነው።  ክርስትናም በተጋድሎ ሕይወት በመትጋት ሥጋን በቀንና ሌሊት ለነፍስ እንዲገዛ በማድረግ የሚኖር ሕይወት ነው።  ጌታችን ሐዋርያቱን “ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ” ባለው መሠረት ቤተክርስቲያንም በቀንና በሌሊት በኪዳኑ በቅዳሴው በማህሌቱ እግዚአብሔርን ታመሰግናለች፡፡ ለኒቆዲሞስ በሌሊት ገስግሶ ወደ ጌታችን መምጣት ልጅነትን ለምናገኝበት የምሥጢረ ጥምቀት ትምህርት እንደተገለጠለት እኛም በሌሊት በነግህ ጸሎት በመትጋት ረቂቅ የሆነውን መንፈሳዊ ዕውቀት ሰማያዊ ምሥጢር ይገለጥልናል። እኛም ኒቆዲሞስን አብነት አድርገን ከዚህ የፈተና ዓለም ለማምለጥ በኦርቶዶክሳዊ ሰውነት እንድንጸና በትጋት ወደ ቤተ ክርስቲያን በቀንና በሌሊት ልንገሰግስ በኪዳኑ በማኅሌቱ በቅዳሴው ጸሎት ልንሳተፍ ያስፈልጋል።

፪. ጽንዐ ሃይማኖት (በሃይማኖት መጽናት) – ኒቆዲሞስ እስከ መጨረሻው በመጽናት የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውን በንጹሕ የተልባ እግር በፍታ ገንዞ በአዲስ መቃብር፣ በጌቴሴማኒ የቀበረ (ዮሐ ፲፱፥ ፴፰) ለታላቅ ክብር በመብቃት እስከመጨረሻው በመታመን አርአያችን ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለደቀ መዝሙሩ ጢሞቴዎስ በላከው በ፪ኛይቱ መልእክቱ እንደገለጸው ክርስትና በጅምር የሚቀር ሳይሆን እውነትን ሳንፈራ በመመስከር በተጋድሎ የምናሳልፍበት ለፈጸሙትም የድል አክሊል የሚያገኙበት ሕይወት ነው (፪ጢሞ ፬፥፰)። መከተል ብቻ ሳይሆን መታመንም እንደሚገባ ካሳዩን አንዱ ኒቆዲሞስ ነው። በዚህም በጌታችን ትምህርት ተስበው ተአምራቱን በማየት ከተከተሉት ሰዎች ውስጥ በቀራንዮ የተገኙት ጥቂቶቹ ውስጥ የሆነው ኒቆዲሞስም ከጌታችን በተማረው ትምህርት ጸንቶ በመኖር በሃይማኖት መጽናትን ያሳየን። ቀራንዮ የምግበ ነፍስ ቦታ ናትና ኒቆዲሞስም ፈተናን ሳይሰቀቅ እስከ መጨረሻው የጸና ጻድቅ ነው። የክርስትና አገልግሎት ሲመቸን የምንሳተፍበት ፈተና ሲበዛ የምንሸሽበት አይደለም። የሃይማኖቱ ጽናትም በተግባር የተፈተነ ነው። ኒቆዲሞስ ከሐዲስ ኪዳን ካህናት ቀድሞ የጌታችንን ነፍስ የተለየው መለኮት የተዋሐደው ክቡር ሥጋ ለመገነዝ የበቃ አባት ነው። የጌታችንን ክቡር ሥጋ ገንዘው ሲቀብሩም በጸናች የተዋሕዶ እምነት ጌታ እንደገለጠላቸው “ቅዱስ እግዚአብሔር፣ ቅዱስ ኃያል፣ ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት” የሚለውን ቤተ ክርስቲያናችን እስከ ዕለተ ምጽአት የክርስቶስን ሥጋና ደም ስትባርክ የምትጠቀምበትን ጸሎት እስከ ፍፃሜው እየጸለዩ ነበር። በዚህም ኒቆዲሞስ ከሐዲስ ኪዳን ካህናት ቀድሞ ምሥጢረ ጥምቀትን ከጌታ እንደተማረ፣ የሐዲስ ኪዳንን የምሥጢራት አክሊል ምሥጢረ ቁርባንንም እንዲሁ ተማረ። ይህንንም በሚመለከት ሊቁ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ አብሮት ይቀድስ የነበረውን ንፍቅ ካህን በባረከበት አንቀጽ “በዚህ ምሥጢር እየተራዳኝ ከእኔ ጋር ያለ ይህንን ካህን እርሱንም እኔንም ሥጋህን እንደገነዙት እንደ ዮሴፍና እንደ ኒቆዲሞስ አድርገን” (ቅዳሴ ማርያም ቁጥር ፻፲ወ፭) ብሏል።

፫. አትሕቶ ርዕስ (ራስን ዝቅ ማድረግ) – ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ (፫÷፩)፣ መምህረ እስራኤል (፫÷፲)፣ ምሁረ ኦሪት (፯÷፶፩) ሲሆን ራሱን ዝቅ አድርጎ የተማረ የትሕትና አርአያነትን እንማራለን።  በዚያን ዘመን በእርሱ ደረጃ የነበሩ ታላላቅ የአይሁድ ምሁራን መንፈሳዊ ሥልጣናቸውና ሹመታቸው የእግዚአብሔር ስጦታ መሆኑን ረስተው በሕዝቡ ላይ የሚመጻደቁ በጌታችንም ላይ የሚዶልቱበት የሚሳለቁበት ሕጋችን ተሻረ በማለት እውነተኛዋን ትምህርት ለመቀበል ያልወደዱበት እንዴውም ወደ ጌታ ትምህርት የሚሄዱትን የሚነቅፉበት እነርሱም የሚያምጹበት ሰዓት ነበር። ጌታችንም የፈሪሳውያን ሀሳባቸው በግብዝነት የተሞላና ከንቱም እንደሆነ ነግሯቸዋል። ለደቀመዛሙርቱም ከጻፎችና ከፈሪሳውያን እርሾ ተጠበቁ እያለ አስጠንቅቋቸዋል። መልካም ሥራም ማድረግ እንዳለባቸው ስለ ህጉም አስተምሯቸዋል (ማቴ ፭ ፥፳፣ ማቴ ፲፮፦ ፮)። ኒቆዲሞስ ግን ከእነዚህ ከፈሪሳዊያን መካከል የተገኘ ልዩ ምሁረ ኦሪት ኒቆዲሞስ ራሱን ለእውነት ልቡን ለእምነት አዘጋጅቶ ከዅሉ ቀድሞ በሌሊት ክርስቶስን ፍለጋ የመጣ ከእነዚህ ፈሪሳዊያን ወገን ተለይቶ እንደ አባታችን አብርሃም ወደ ጽድቅ መንገድ የተጠራ ነው።  ሹመት እያለው (የአይሁድ የምክር ቤት አባል ሆኖ) ሁሉ ሳይጎድልበት እውነትን ለማወቅ ሊቅነቱ ሳይታሰበው ከአካባቢው ጋር መመሳሰልን ሳይመርጥ ራሱን ዝቅ አድርጎ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሊማር በሌሊት መጣ። መምህረ ትሕትና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የኒቆዲሞስን ትሕትናውን ተቀብሎ “ለምን በቀን አትመጣም?” ሳይለው እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ትውልድ ሁሉ የሚማርበትን ረቂቁን ምሥጢረ ጥምቀትን አስተማረው።

፬. አልዕሎ ልቡና (ልቡናን ከፍ ከፍ ማድረግ) – ኒቆዲሞስ የምሥጢረ ጥምቀት ( ዳግመኛ የመወለድን ምሥጢርን) ለማወቅ ልቡናውን ከፍ ከፍ አደረገ (ዮሐ ፫÷፩-፳፩)። መጽሐፍ እንደሚነግረን ኒቆዲሞስ በመጀመርያ የጥምቀትን ነገር ሲሰማ ለመቀበል ተቸግሮ ነበር። ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ኅብረት ወጥቶ በትሕትና ወንጌልን ለመማር በሃይማኖት ልቡናውን ለእግዚአብሔር ቃል አዘጋጀ። ለአብርሃም የግዝረትን ጸጋ የሰጠ ጌታ በትሕትና ለቀረበው ኒቆዲሞስ የግዝረት ጸጋ ፍጻሜ የሆነች የልጅነት ጥምቀትን ነገር አስተምሮታል፡፡ ነገር ግን ጌታችን የኒቆዲሞስን አመጣጥ በማየት ልቡናውንም ከፍ ከፍ ስላደረገ ምሥጢረ ጥምቀትን ገለጸለት። ሊቁ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በሥርዓተ ቅዳሴ ምእመናንን በማነቃቃት ልቡናቸውን ከፍ እንዲያደርጉ “አልዕሉ አልባቢክሙ [ልቦናችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ]” ብሎ የሚያዘው ምእመናን የቅዱስ ሥጋውና የክቡር ደሙ ምሥጢር እንዲገለጽልን፣ ከሥጋዊው መብል ሃሳብ ወደ ሰማያዊው መብል ልቡናችንን እንድናነሣ ሲያሳስብ ነው። ምእመናንም በጸሎተ ቅዳሴ ካህኑ የቅዱስ ኤጲፋንዮስን ትእዛዝ ሲያሰማ “በአምላካችን በእግዚአብሔር ዘንድ አለን” በማለት እንመልሳለን። ይሄም የኒቆዲሞስ ትጋት አርአያነት እኛም ክርስቲያኖች በጸጋ የተሰጡንን ስጦታዎቻችንን እንድናውቅ ልቡናችንን ከፍ ከፍ አድርገን በመንፈሳዊ እውቀትና ልዕልና፣ የእግዚአብሔርን ፈቃድ በመረዳት፣ እንዴት በጽድቅ መመላለስ እንዲገባንና ስለምንወርሳት መንግሥተ ሰማይ መማር ማወቅ እንዳለብን ያስረዳናል፡፡ “ቅዱሱን ማወቅ ማስተዋል ነው” ተብሎ በምሳሌ መጽሐፍ እንደተጻፈ (ምሳ ፱፥፲፩)

፭. ስምዐ ጽድቅ (የእውነት ምስክርነት) – ኒቆዲሞስ ማንንም ሳይፈራ እውነትን በመመስከር ጌታችንን የሚከሱትን በእውነት መንገድ የሚሄዱትን አይሁድን አሳፈራቸው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እኔ ለእውነት ለመመስከር መጥቻለሁ” በማለት እውነትን እንድንመሰክር አብነት ሆኖናል (ዮሐ.፲፰፥፴፯)። በተጨማሪም “በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው አባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ። በሰው ፊት የሚክደኝን ሁሉ ደግሞ በሰማያት ባለው አባቴ ፊት እክደዋለሁ” ሲል ስለ ሃይማኖታችን እውነትን መመስከር እንደሚገባን አስተምሮናል (ማቴ.፲፥፴፪-፴፫)፡፡ እንዲሁም ለኒቆዲሞስ ሲያስተምረውም “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ የምናውቀውን እንናገራለን ያየነውንም እንመሰክራለን” በማለት ለእውነት መመስከር እንደሚገባ አስገንዝቦታል (ዮሐ ፫÷፲፩)።  በዚህም ኒቆዲሞስ ከጌታው የተማረውን በአይሁድ ፊት ሳይፈራ እና ሳያፍር ሥለ እውነት ሲመሰክር “ከእነርሱ አንዱ በሌሊት ቀድሞ ወደ እርሱ መጥቶ የነበረ ኒቆዲሞስ ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን? አላቸው። እነርሱም መለሱና፡- አንተም ደግሞ ከገሊላ ነህን? ነቢይ ከገሊላ እንዳይነሣ መርምርና እይ አሉት። እያንዳንዱም ወደ ቤቱ ሄደ።” በማለት ገልጾታል (ዮሐ ፯፥፶-፶፪)።  ምሁረ ኦሪት ነውና ካህናቱን መጽሐፍ ጠቅሶ እውነትን ተናግሮ አሳፍሯቸዋል።  በመሪዎች ፊት በታላላቅ ሰዎች ፊት እውነትን መመስከር ክርስትናችን የሚያስገድደን ቁም ነገር ነው (ሉቃ ፲፪፥ ፰)።  ቤተክርስቲያን “ሰማዕታት” እያለች የምትዘክራቸው ቅዱሳን በሙሉ ለእውነት ብለው ራሳቸውን ለክርስቶስ አሳልፈው የሰጡ ናቸው። በፍርሐትና በሀፍረት በይሉኝታና በሀዘኔታ እውነትን አለመመስከር በክርስቶስ ፊት ያስጠይቃል እንጂ አያስመሰግንም (ማቴ ፲፥፴፪)። ሐዋርያው “ለእውነት እንጂ በእውነት ላይ ምንም ማድረግ አንችልም” እንዳለ እኛም እንደ ኒቆዲሞስ የእውነት ምስክሮች እንሁን (፪ቆሮ ፲፫፥፰)። ስለዚህም ነው ይሄንን ሳምንት ኒቆዲሞስ ብለን ናከብር አርአያችን አድርገን የተደረገለትንም ያደረገለትንም በማሰብ ስለ እውነት መመስከር የሚገባን፡፡

አምላከ ኒቆዲሞስ ልዑል እግዚአብሔር ለኒቆዲሞስ ምሥጢሩን ገልጾ እንዳዳነው እና እንዳከበረው ለእኛም ምሥጢሩን ይግለጽልን፤ ማስተዋሉን አድሎ የተማርነውን አጽንተን እስከ መጨረሻው ድረስ ታምነን በጥበብ በሞገስ በምግባር በሃይማኖት ጸንተን ስሙን ለመቀድስ ክብሩን መንግሥቱን ለመውረስ ያብቃን ጥበቡን ያድለን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

ምንጭ፦ 

፩. ወንጌል አንድምታ ትርጓሜ

፪. ጾመ ድጓ ዘቅዱስ ያሬድ

፫. መዝሙረ ዳዊት አንድምታ ትርጓሜ

፬. https://eotcmk.org

 

በኢ/ኦ/ተ/ቤ/በሰ/ት/ቤቶች/ ማ/መ/ማ/ቅ ሩቅ ምሥራቅ ማእከል ሚዲያ እና ሕዝብ ግንኙነት ክፍል

መጋቢት ፳፰ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም

ቻይና

 

መኑ ውእቱ ገብርኄር ?

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ዘለዓለም ሥላሴ!

ገብር ኄር

ስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት “ገብር ኄር” ተብሎ ይጠራል።  ቃሉ “ገብር” እና “ኄር” ከሚሉ ከሁለት የግእዝ ቃላት የተገኘ ሲሆን “ገብር” የሚለው አገልጋይ፣ ሠራተኛ፣ ባሪያ ማለት ሲሆን “ኄር” የሚለው ቃል ደግም መልካም፣ ቸር፣ ጥሩ፣ ደግ የሚል ፍችን ይይዛል። በአንድነት “ገብር ኄር” ማለት “መልካም አገልጋይ ፣ ቸር አገልጋይ፣ ታማኝ አገልጋይ” ተብሎ ይተረጎማል። ይህ ጽንሰ-ሀሳብ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በስፋት የሚንጸባረቅ ሲሆን በተለይም በሐዲስ ኪዳን ውስጥ የአገልጋይነትን ትርጉም እና ክርስቲያኖች እንዴት ለእግዚአብሔር እና ለሌሎች ሰዎች ታማኝ አገልጋዮች መሆን እንደሚችሉ ያሳያል። ስድስተኛው ሰንበት “ገብር ኄር” ተብሎ የሚጠራበት ምክንያት በዚሁ ሰንበት የሚዘመረው የቅዱስ ያሬድ ጾመ ድጓ ከዋዜማው ጀምሮ የሚከተሉትን ስለሚጠቅስ ነው።

⇛ “ገብር ኄር ወገብር ምእመን ገብር ዘአሥመሮ ለእግዚኡ ትርጉሙ፦ ጌታውን ያስደሰተው አገልጋይ ታማኝና ቸር አገልጋይ ነው።

⇛ “ገብር ኄር ወገብር ምእመን ዘበውሕድ ምእመነ ኮንከ ዲበ ብዙኅ እሰይመከ ትርጉሙም፦ በጥቂቱ የታመንክ ቸር አገልጋይ ሆይ፥ በብዙ እሾምሃለሁ።

⇛ “ዘበምልክናከ ሠናየ ገበርከ ብፁዕ አንተ ገብርኄር ትርጉሙም፦ በሹመትህ በጎ የሠራህ ቸር አገልጋይ ሆይ፥ ብፁዕ ነህ።

⇛“ዘይረክቦ ለእግዚኡ በምግባረ ሠናይ ወይሰይሞ ዲበ ኩሉ ንዋዩትርጉሙም፦  በደግ ሥራ ጌታው የሚያገኘውና በገንዘቡ ሁሉ ላይ የሚሾመው ቸር እና የታመነ አገልጋይ ማን ነው

⇛ “ለአግብርት ግዕዛን ለማሃይምናን ሰላም ዛቲ ዕለት ሰንበተ ክርስቲያን ትርጉሙም፦ ይህች ዕለት የክርስቲያን ሰንበት ለአገልጋዮች ነፃነት ለአማኞች ሰላም ናት።

⇛ “ኩኑ እንከ ከመ አግብርት ኄራን ወከመ አግብርተ ክርስቶስ ምእመናን እለ ይጸንሑ ለእግዚኦሙ እስከ የአቱ እምከብካብ ዘበሰማያት ትርጉሙም፦ እንግዲህ በሰማይ ወዳለው መንግሥተ እግዚአብሔር እስክትገቡ ድረስ ጌታችሁን ደጅ እንደሚጠኑ እንደ ቸር አገልጋዮችና እንደ ክርስቶስ ታማኝ አገልጋዮች ሁኑ።

⇛ “ጹሙ ወጸልዩ ከመ አግብርት ተቀነዩ ትርጉሙም፦ እንደ መልካም አገልጋዮች ጹሙ ጸልዩ ለእግዚአብሔር ተገዙ።

በእነዚህ መዝሙራትና ቃላት አማካኝነት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የካህናትንና የምእመናንን የጽድቅ ሥራ ከመልካም አገልጋይ ሥራ ጋር እያነጻጸረ፥ የኃጥአንን የበደል ሥራ ደግሞ በተቃራኒው እያመላለሰ በወንጌል ያስተማረውን ትምህርት ያስታውሳል። በአጠቃላይም ስለ ጻድቃንና ኃጥአን በምሳሌ የተናገረውን ቃለ ወንጌል እየጠቃቀሰና እያነሳሳ ስለሚዘመር፥ ይህ ሰንበት ገብርኄር ተብሎ ይጠራል። ሰለዚህ ይህ ሰንበት የፃድቅ መታሰቢያ ዕለት ነው። በዚህ ዕለተ ሰንበት መታሰቢያነት የተሰጠውን የገብርኄርን የምሳሌ ትምህርት የምናገኘው ቀጥሎ በተጠቀሱት የወንጌል ክፍሎች ነው።  ማቴ ፳፭፥፲፬-፵፮ ፤፲፫፥፲፪ ሉቃ ፲፱፡፲፪-፳፯

 

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ እንጂ ያለ ምሳሌ አያስተምርም። አንቀጸ አባግዕን ሲያስተምር የሙሴን በጎች እያሰበ ነበር። አንቀጸ ብፁዓንን ሲያስተምር በብሔረ ብፁዓን ያሉ ይህንን ዓለም የናቁ ከዓለም የራቁ የብፁዓን አበውን ሕይወት ጠቅሶ ነበር። እነዚህ ብፁዓን ከባቢሎን ምርኮ በኋላ ከኢየሩሳሌም ተውጣጥተው በነቢዩ ዕዝራ መሪነት ብሔር ብፁዓን የገቡ ሲሆኑ እስከዛሬ ድረስ በሕይወት ያሉ መልአከ ሞት የማያስደነግጣቸው ናቸው። እኒህም ኄራን ብፁዓን ይባላሉ። ጌታችን ይህን በምሳሌ አንሥቶ ስለ ደጋግ ባሮች ሲያስተምረን “ወደ ሌላ አገር የሚሄድ ባለ ጸጋ ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደ ሰጣቸው እንዲሁ ይሆናል። ለእያንዳንዱ እንደ አቅሙ ለአንዱ አምስት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ አገር ሄደ። አምስት መክሊት የተቀበለው ሄዶ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ። እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ። አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፍሮ የጌታውን ገንዘብ ቀበረ። ከብዙ ዘመን በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው።” ማቴ ፳፭፥፲፬-፳

ባለጸጋው ማን ነው?

እዚህ ላይ ባለጸጋው እግዚአብሔር አምላካችንን ይመስላል። አገልጋዮቹ ደግሞ እኛ ክርስቲያኖች ነን። ለሰዎች ሁሉ ጸጋን፣ ስጦታን  የሚሰጥ ጌታ ለአገልጋዮቹ እንደ አቅማቸው አምስት፣ ሁለትና አንድ መክሊት ሰጣቸው። መክሊት የተባለው የአገልግሎት ጸጋ ምሳሌ ነው። ጌታችን ለእያንዳንዱ እንደ አቅሙ የአገልግሎት ጸጋ ይሰጣልና። አገልጋዮቹ ደግሞ የአገልግሎት ጸጋ የተቀበሉና ምእመናንን በመንፈሳዊ ሥርዓት የሚያገለግሉ ካህናትና  በልዩ ልዩ ጸጋ የሚያገለግሉ ምእመናን ምሳሌ ናቸው። ጌታ  አምስት ለሰጠው ሁለት፣ ሁለት ለሰጠው አንድ፣ አንድ ለሰጠው አምስት መስጠት ተስኖት ሳይሆን እንደ ችሎታቸው ለመስጠት ነው። ጌታችን ለእኛም እንደ አቅማችን የአገልግሎት ጸጋ ሰጥቶናል። ሁለት የተሰጠው ለምን አምስት አልተሰጠኝም አይበል፣ ይልቁንስ በተሰጠው ይታመን፤ በተሰጠው ታምኖ ሲያገለግል ይጨመርለታልና። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “መንፈስ ቅዱስ አንድ ሲሆን ስጦታው ልዩ ልዩ ነው፤ ጌታም አንድ ሲሆን ልዩ ልዩ አገልግሎቶች አሉ። ሁሉን በሁሉ የሚያደርግ እግዚአብሔርም አንድ ሲሆን ልዩ ልዩ አሠራር አለ ለሁሉም ጌታ እየረዳ በየዕድሉ እንደሚገባውና እንደሚጠቅመው ለእያንዳንዱ በግልጥ ይሰጠዋል።” (፩ኛ ቆሮ. ፲፪፥፬-፯) እንዳለ ሁላችንም በተሰጠን  ጸጋ መጠን እንድናገለግል መክሊት ተቀብለናል።

“አገልጋዮቹንም ጠርቶ ሊያተርፉበት ገንዘቡን ሰጣቸው” እንደተባለ ሁላችንም በተሰጠን ጸጋ ማትረፍ መቻል አለብን።  ይህም ማለት የተሰጠንን መንፈሳዊ ዕውቀት፣ ጸጋ ለሌሎች ማካፈል፣ በዚያም ከራሳችን አልፈን ለሌሎች የድኅነት ምክንያት መሆን ማለት ነው። “ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ተመልሶ ተቆጣጠራቸው” እንዲል ጌታችን እግዚአብሔር አገልጋዮችን እንደ አቅማችን የምናገለግል ሁላችንንም በተሰጠን መክሊት ምን እንዳተረፍንበት ሊቆጣጠረን ይመጣል። አምስት መክሊት የተቀበለው ታማኝ አገልጋይ ሄዶ፣ ነግዶ፣ ወጥቶ ወርዶ ሌላ አምስት መክሊት አተረፈ፤ ሁለት የተሰጠውም እንዲሁ በድካም፣ በመታዘዝ ሌላ ሁለት አተረፈ። እነዚህ አገልጋዮች የተሰጣቸውን እንደ ችሎታቸው አትርፈዋልና መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርሱ በሚያስረዳ ምሳሌ “አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” እየተባሉ ተመሰገኑ።

ይህንን ቃል ሊቃውንቱ ሲተረጉሙት፦ አምስት መክሊት በቁሙ ገንዘብ አይደለም። ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ነው ይላሉ። እነዚህ ሀብታት ልዩ ልዩ ሲሆኑ በዚህ ወንጌል  ውስጥ ባለ አምስት መክሊት የተባሉት ነቢያት ናቸው። አምስት የተሰጠው ሌላ አምስት አትርፎ ዐሥር እንዳደረገው ሁሉ ነቢያትም በብሉይ ኪዳን ጌታችንን ይወርዳል ይወለዳል ብለው ትንቢት ተናግረው በሐዲስ ኪዳን ትንቢት የተናገሩለት ጌታችን ተወልዶላቸው አስበ ትንቢታቸውን ተቀብለው ገነት ገብተዋል። ትርፋቸው ገነት መግባት ነውና። ከነቢያቱ መካከል ሊቀ ነቢያት ሙሴን መጥቀስ እንችላለን። ሙሴ ጌታችን ይወርዳል ይወለዳል ከማለቱ በተጨማሪ አምስት መጻሕፍትን ጽፏል። ባለ አምስት መክሊቱ ሌላ አምስት መክሊት አትርፎ ዐሥር ባደረገ ጊዜ፦  “ጌታውም፡ መልካም፥ አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።”ማቴ ፳፭፥፳፩። ባለ አምስት መክሊቱ ሌላ አምስት ባተረፈ ጊዜ በብዙ ወገን ይሾማል። ይህ ባለ ብዙ ወገን ሲመት የመንግሥት ሢመት ነው። ከፍጥረተ ዓለም እስከ ሕልቀተ ዓለም ያሉ ምእመናን በሙሉ አምስት ተሰጥተው ሌላ አምስት ካተረፉ መንግሥተ ሰማይ ቤታቸው ናት።

በሁለት መክሊት የተመሰለው ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ነው። የመንፈስ ቅዱስ ሀብቱ ብዙ ነው። ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ጴጥሮስን ለዚህ እንደ አብነት ይጠቅሱታል። ሁለቱ መክሊት የተባሉት ደግሞ ብሉይ እና ሐዲስ ኪዳን ናቸው። ይህም ማለት የቀለም መምህርነቱ ሲገለጽ በመንፈስ ቅዱስ ተገልጦለት ምሥጢረ ሰማይ ወምድርን ከተረዳ በኋላ ለጊዜው ለቀለሜንጦስ አስተምሯል። ሊቃውንቱ ጨምረውም እኒህን መክሊት በመዓረግ ሲተረጉሙት ደግሞ፦ ባለ አምስት መክሊት የተባሉት ሊቃነ ጳጳሳት ናቸው። አምስቱ ሀብታት ደግሞ አንብሮተ እድ፣ ቀሳውስትን እና ዲያቆናትን መሾም፣ ጥምቀት እና ቁርባን ናቸው። ሊቀ ጳጳሱ በአንብሮተ እድ ይሾማል። አሐዱ ብሎ አሕዛብን ያጠምቃል። ከዚያ ቀድሶ ያቆርባል። እኒህ አምስቱን መክሊቶች ይፈጽማል። በዚህ ጊዜ ገብር ኄር ተብሎ በጌታችን ቃል ተወድሶ መንግሥተ ሰማይን ይወርሳል። ባለ ሁለት መክሊት የተባሉት ደግሞ ካህናት ናቸው። እኒህ መክሊቶች ደግሞ ጥምቀት እና ቁርባን ናቸው። ባለ ሁለት መክሊቱ ሌላ ሁለት አትርፎ በተገኘ ጊዜ “መልካም፥ አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” እንዳለው የተሰጣቸውን መክሊት በአግባቡ ተጠቅመው ያተረፉ ቤታቸው ገነት መንግሥተ ሰማያት ናት።

“አንድ መክሊትም የተቀበለው ቀርቦ ጌታ ሆይ፥ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደ ሆንህ አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ መክሊትህ አለህ አለ። ጌታውም መልሶ አንተ ክፉና ሰነፍ ባሪያ፥ ካልዘራሁበት እንዳጭድ ካልበተንሁበትም እንድሰበስብ ታውቃለህን?” የተሰጠውን የአገልግሎት ጸጋ እንደ አቅሙ ከመጠቀም ይልቅ የመናፍቃንን ክርክርና ሥም ማጥፋት፣ የዓለምን ፈተና፣ የሥጋውን ምኞት መቋቋም አቅቶት መክሊቱን ቀበረው። ጌታው ሲጠይቀው ግን የተገለጠ ድካሙን ከማስተዋል ይልቅ በሐሰት ቃል ጌታውን ወቀሰው። ሰነፍ አገልጋዮች ሁሌም እንዲህ ናቸው፤ ለስንፍናቸው ሌሎችን ተጠያቂ ያደርጋሉ እንጂ ወደራሳቸው ተመልክተው ስሕተታቸውን አያርሙም። ይህ አሁን በዓለም ያሉ አገልጋዮችን ይመለከታል። ብዙ መክሊትን በመቅበር ይታወቃሉና። ሊቃውንቱ ይህን ሲያብራሩ በባለ አንድ መክሊት ተመስሎ የቀረበው ይሁዳ ነው ብለው ይተረጉሙታል። እንደ እነ ጴጥሮስ ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብሎ ተምሮ ነበር። የተማረውን ማስተማር ስላልቻለ እና በሃይማኖቱ ጸንቶ ስላልኖረ  መንግሥተ ሰማይን አልወረሰም። ለይሁዳ መክሊቱ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብሎ የተማራት ወንጌል ነበረች እርሷኑ ቀብሯት ቀርቷልና። ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መክሊቱን በመዓረግ ሲተሩጉሙት ባለ አንድ መክሊት የተባለው ዲያቆን እንደሆነ ይናገራሉ። ይህቺውም ተልእኮ ናት። አንድም ባለ አምስት ጥምቀት፣ ተአምኖ ኃጣውእ፣ ተባሕትዎ፣ ምንኲስና እና ከዊነ ሰማእት ናቸው። ባለ ሁለት ደግሞ ጥምቀት እና ተአምኖ ኃጣውእ ሲሆኑ ባለ አንድ ደግሞ ጥምቀት ናት። አንድም ባለ አምስት አሚን፣ ተስፋ፣ ምሕረት፣ ትዕግሥት፣ ፍሥሐ ናቸው። ባለ ሁለት ደግሞ አሚን እና ተስፋ ሲሆኑ ባለ አንድ ደግሞ አሚን ነው። አንድም ባለ አምስት ፍጹም ባለ ጸጋ፣ ባለ ሁለት በመጠኑ ባለ አንድ ፍጹም ድኃ ነው።

ቸር አገልጋይ ማነው?

ቸር አገልጋይ ማለት ለጌታው የታመነ፣ የተሰጠውን መክሊት ያላስቀረ፣ ነገር ግን ያተረፈና የጨመረ፣ በዚህም ምክንያት ወደ ጌታው ደስታ የገባ ነው። ከዚህ በተቃራኒ ጌታውን የተሳደበውና በእርሱ ላይ ያመፀው አገልጋይ በባዶ እጁ ወደ ዘላለማዊ ጨለማ ይጣላል።

ጸጋና በረከት

እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ልጁ ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ጸጋዎችን ይሰጣል። ይህ ጸጋ በጎ ሥራ እንድንሠራ ይረዳናል፣ ብዙ በረከትንም ያስገኛል። ይህ ጸጋ የምናገኘው ከምሥጢራተ ቤተክርስቲያን በመሳተፍ፣ ዕለት ዕለት ከቅዱስ ቁርባን በመቀበል እና ከሌሎችም ምሥጢራት ነው። እነዚህ ምሥጢራት የእግዚአብሔር ታማኝ አገልጋዮች እንድንሆን ይረዱናል።

መንግሥተ ሰማያት

በመጨረሻም ታማኝ ሆነን ብንገኝ መንግሥተ ሰማያትን እንወርሳለን። “ሥጋዬን የበላ ደሜንም የጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው” (ዮሐ. ፮፥፶፬) የሚለው የእግዚአብሔር ቃል እውነት ነው። ከመሬት የፈጠረው አምላክ ጌታው የሰነፍ ገንዘብ አዳምን መሬት ነህና ወደ መሬት ተመለስ ይለዋል። “ለመክሊተ ሀካይ አዳም ይቤሎ እንተፈጠሮ መሬተ ውስተምድር ለትባዕ አምጣነ መሬት አንተ [እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ከመሬት ፈጥሮ በተሳሳተ ጊዜ ቀድሞም መሬት ነህና ወደ መሬትነትህ ተመለስ]” ያለውን በሰሙ ያስታውሰናል በወርቁ ደግሞ ስንመለከተው ገብር ሐካይ የተባለው የተቀበለውን አንዲት ወርቅ መሬት ውስጥ ቀብሮ ማስቀመጡን የሚገልፅ ነው።

የማያተርፍ አገልጋይ

ከመጀመሪያው ጀምሮ የእግዚአብሔር ልጅነት የሌለው ግን በምድርም በሰማይም ሐዘን ይሆንበታል። መንግሥተ ሰማያትን መውረስ ቀርቶ ወደ ዘላለማዊ ጨለማ ወደ ጥርስ ማፋጨት ይጣላል።

በመጨረሻም  ቸር አገልጋይ መሆን ታማኝነትን፣ ኃላፊነትን እና የተሰጠንን ጸጋ በአግባቡ መጠቀምን ይጠይቃል። ስለዚህ፥ ወንድሞችና እኅቶች፥ ሁላችንም በሕይወታችን የምንችለውን መልካም ሥራ ሠርተን ወደ ጌታችን ደስታ ለመግባት እንትጋ። አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቸርነቱ ይርዳን!!

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር!

ምንጭ፦ 

  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ድረ-ገፅ
  • ከሣቴ ምሥጢር (በመምህር አባ ኃይለመለኮት ይኄይስ)
  • ወንጌል ቅዱስ በአንድምታ ትርጉም

በኢ/ኦ/ተ/ቤ/በሰ/ት/ቤቶች/ ማ/መ/ማ/ቅ ሩቅ ምሥራቅ ማእከል ሚዲያ እና ሕዝብ ግንኙነት ክፍል

መጋቢት ፳፩ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም

ቻይና

ድልዋኒክሙ ንበሩ [ተዘጋጅታችሁ ኑሩ]! ማቴ ፳፬፥፵፬

እንኳን ለዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ደብረ ዘይት በሰላም አደረሳችሁ/አደረሰን።  

የዚህ ጽሑፍ መሠረታዊ ዓላማ፡

  • የደብረ ዘይትን ምንነት ማስረዳት (ስያሜ፣ የት፣ መቼ፣ ለምን)? ፤
  • ጌታችን በደብረ ዘይት ቅዱሳን ሐዋርያትን ምን እንዳስተማራቸው መማር፤
  • አምላካችን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ያስተማራቸውን የዳግም ምጽአት ምልክቶች ማሳወቅ ፤
  • ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም በግርማ መለኮት፣ በክበበ ትስብእት፣ በይባቤ መላእክት ኅብረት እንዲኖረን ተዘጋጅተን መጠበቅ እንዳለብን መጠቆም ፤
  • ማጠቃለያ፣ ጸሎት

ደብረ ዘይት ከሁለት ቃላት የተገኘ ሐረግ ነው። “ደብር” ማለት “ተራራ፣ ጋራ” ማለት ሲሆን «ዘይት» ማለት ደግሞ «ወይራ፣የተክል ዕንጨት» ማለት ነው። ስለዚህ “ደብረ ዘይት” ማለት የወይራ ዛፍ የሞላበት፣ የበዛበት፣ የወይራ ተራራ ማለት ነው። በመኾኑም ደብረ ዘይት የወይራ መብቀያ፣ በወይራ ደን የተሸፈነ ተራራ ማለት ነው። (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ገፅ ፫፻፴፮ና ፬፻፲፱)፣ ኢንሳይኮሎፒዲያ)

የደብረ ዘይት ተራራ በእስራኤል ሀገር ከኢየሩሳሌም ከተማ በስተምሥራቅ ፸፭ ሜትር ርቀት የሚገኝ ሲኾን፣ ባለ ብዙ የኖራ ድንጋይ ሸንተረር ያለበትና በቄድሮን ሸለቆ/ወንዝ ተሻግሮ ፰፻፰ ሜትር ከባሕር ጠለል በላይ ከፍታ ያለው ተራራ ነው። ከግርጌው ጌቴሴማኒ የተባለው የአትክልት ስፍራ ይገኛል። ይህም ተራራ ለመጀመሪያ ጊዜ ከብሉይ ኪዳን የታሪክ መጽሐፍት አንዱ በኾነው በመጽሐፈ ሳሙኤል ካልዕ ላይ ተጠቅሷል ። “ዳዊትም ተከናንቦ ያለ ጫማ እያለቀሰ ወደ ደብረ ዘይት ተራራ ወጣ” (፪ኛ ሳሙ ፲፭፥፴) ። በተጨማሪም ነቢዩ ዘካርያስ ስለመጨረሻው ዘመን በተናገረበት ምዕራፍ ላይ ስለዚህ ተራራ ጽፎ እናገኘዋለን ፤ “በዚያም ቀን እግሮቹ በኢየሩሳሌም ትይዩ በምሥራቅ በኩል ባለው በደብረ ዘይት ላይ ይቆማሉ” (ዘካ ፲፬፥፬ )

ይህም ተራራ (Mount of Olives) ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙ ሥራን ከሠራባቸው ቅዱሳት መካናት አንዱ ነው።ታላላቅ ምሥጢራት የተከናወኑበት፣ ለደቀመዛሙርቱ ትምህርት የሰጠበት፣ ስለ ምሥጢረ ምጽአቱ ያስተማረበት፣ ወደ ሰማይ ያረገበትና ዳግመኛ ለፍርድ የሚመጣበት ተራራ ነው። በዚሁ ተራራ ላይ ቀን በከተማና በገጠር ሲያስተምር ውሎ ሌሊት የሚያድርበት የኤሌዎን ዋሻ ይገኛል። (ሐዋ ፩፥፲፪ ፤ ሉቃ ፳፬፥፶)

ማኅቶተ ቤተክርስቲያን ማኅሌታይ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ የዐቢይ ጾም እኩሌታ ያለውን ሰንበት በዚህ ተራራ ስም ሰይሞታል።  በዚህም ዕለት ስለ ጌታችን ዳግም ምጽአት በስፋት ይሰባካል።  “እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይምጽእ፤ ወአምላክነሂ ኢያረምም፤ እሳት ይነድድ ቅድሜሁ [እግዚአብሐር ግልጥ ሆኖ ይመጣል፤አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነድዳል]” መዝ ፵፱፥፫ እግዚአብሔር በግርማ መለኮት፣ በክበብ ትስብእት፣ በይባቤ መላእክት ለጻድቃን ሊፈርድላቸው፣ በኃጥአን ሊፈርድባቸው ይመጣል፣ መጥቶም ዝም አይልም ጻድቃንን ንዑ ኀቤየ ብሎ ይጠራል ፣ ኃጥአንን ሑሩ እምኔየ ብሎ ያሰናብታል፤ በፊቱም እሳት ይነድዳል፣ በዙሪያውም ጥልቅ ነፋስ አለ ማለት ጻድቃን የሚድኑበት ሕይወት ኃጥአን የሚጠፉበት መቅሰፍት በባሕርዩ አለ።  ስለዚያ ቀን ሰማያት ተቃጥለው ይቀልጣሉ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኵሳት ይፈታል (፪ኛ ጴጥ ፫፥፲)። በዚያን ጊዜ ከመጀመሪያዉ ሰው ከአዳም ጀምሮ እስከ መጨረሻው ሰው ድረስ ሁላችንም በሕይወተ ሥጋ በነበርንበት ጊዜያችን የሠራነዉን ሥራ ይዘን በፊቱ እንቀርባለን (፪ቆሮ.፭፥፲)። ጌታችንም በጎ የሠሩትን ቅዱሳን በቀኙ፤ ክፉ የሠሩትን ኃጥአንን በግራው ያቆማቸውና ፍርዱን ያስተላልፋል (ማቴ. ፳፭፥፴፩ እስከ ፍጻሜ)። የወጉትም ያዩታል እንደተባለ (ራዕ ፩፥፯)፣ በዚያን ጊዜ በእርሱ ላይ የፈረዱበት፣ በቅዱሳንም ላይ መከራን ያጸኑ ሞትንም የፈረዱ ሁሉ ለፍርድ ይቀርባሉ ሁሉን ትተው የተከተሉት፣ ስለ እርሱ መከራን የተቀበሉ፣ ሞትም የተፈረደባቸው ደግሞ በፍርድ ወንበር ተቀምጠው ይፈርዳሉ (ማቴ ፲፱፥፳፷)። በዚህ ሳምንት ስለ ዳግም ምጽአትና ስለዓለም ፍጻሜ ምልክቶች በስፋትና በምልአት ትምህርት ይሰጣል፥ ይሰበካል ። በዕለቱ የሚነበበው የወንጌል ክፍልም ማቴ ፳፬፥፩-፴፮ ነው።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመቅደስ ወጥቶ ወደ ደብረ ዘይት በሄደበት ሰዓት ደቀ መዛሙርቱ አጠገቡ ቀርበው ዘሩባቤል ያሳነፀውን የመቅደስ ግንቦች እያሳዩት ቀረቡ። የጥዋት ፀሐይ አርፎበት ያሸበረቀውን ቤተመቅደስ ምን ዓይነት ጥበበኛ ሠራው እያሉ እያደነቁ ነበር። አይሁዳውያን ቤተ መቅደሱን የንጉሣቸው ምልክት አድርገው ይመለከቱት ነበር። እግዚአብሔር ክብሩን የሚገልጽበት እና ከምእመናን እጅ መሥዋዕቱን እና መባውን የሚቀበልበት ብቸኛ ቦታ ነው። አይሁዳውያን በየትኛውም ቦታ ቢሆን፣ ፈተና ሲያጋጥመቸው፣ ወደ ቤተመቅደስ ይሄዳሉ፣ ከእግዚአብሔርም ምሕርት ይቅርታን ይለምናሉ፣ እግዚአብሔርም ይባርካቸው ነበር። ለዚህም ነው ደቀ መዛሙርቱ የቤተ መቅደስን ሕንፃ ለጌታ ለኢየሱስ ሊያሳዩት የፈለጉት።(የማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜ በቀሲስ ታድሮስ ማላቲ : Matthew – Fr. Tadros Yacoub Malaty)። ሐዋርያቱ ጌታችንንም አብሮ እንዲያደንቅ ሲጠብቁ አስደንጋጭ ነገር ነገራቸው። ጌታችን ኢየሱስም “ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ  አይቀርም” አላቸው። (ማቴ ፳፬፥፪)። ያ የሚያደንቁት ቤተ መቅደስ እንደሚፈርስ ነገራቸው። ወደ ደብረ ዘይት በደረሱ ጊዜ “ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? ምልክቱስ ምንድን ነው ብለው ጠየቁት። ጌታችንም ይህ መቼ ይሆናል ላሉት ጥያቄ “ስለዚያች ቀንና ስለዚያች ሰዓት ግን ከአባት ብቻ በቀር የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ ልጅም ቢሆን የሚያውቅ የለም” ማቴ. ፳፬፥፴፮ ብሏል። ይህን ማለቱም ሩቅ ቢሆን በየዘመኑ የሚነሡ ክርስቲያኖች ሩቅ ነው ብለው እንዳይዘናጉ ጊዜው ሲቀርብ የሚነሡት ደግሞ ደረሰብን ብለውም እንዳይሸበሩ/እንዳይታወኩ ለመጠበቅም ጭምር ነው። ወልድም አያውቃትም ማለትም ልማደ መጽሐፍ ስለሆነ ነው። አዳም ወዴት ነህ? ከእርሱ እንዳትበላ ብየ ካዘዝኩህ ዛፍ በላህን? (ዘፍ. ፫፥፱፤ ፫፥፲፩)፤ ሰዎች የሰውን ልጅ ምን ይሉታል? እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ? ( ማቴ. ፲፮፥፲፫-፲፭)፤ አልዓዛርን ወዴት ቀበራችሁት? ዮሐ ፲፩፥፴፬ እና ሌሎችንም እያወቀ ያላወቀ አስመስሎ ሲጠይቅ እንመለከታለን። ይህም አላዋቂ ሥጋን እንደተዋሐደ ለማጠየቅ ነው። አንድም በሥራ አላወቃትም ማለት ነው። ይህም ማለት በአብ ልብነት ታስባ በወልድ ቃልነት አልተነገረችም ማለት ነው።

አምላካችን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ምልክቶቹ ከመንገሩ በፊት ማንም እንዳያስታችሁ ተጠበቁ ነበር ያላቸው፣ ቀጥሎም የዳግም ምጽአት ምልክቶች ምን ምን እንደኾኑ፣ ምን ዓይነት ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለባቸው በስፋትና በምልአት አስተምሯቸዋል። የዳግም ምጽአት ምልክቶቹም የቤተመቅደስ መፍረስ፣ የሐሰተኛ ነቢያት መገለጥ፣ የጦርነት እና የተለያዩ አደጋዎች መነሣት ፣ የሰው ልጅ የሚገጥሙት የተለያዩ ችግሮች፣ በቤተመቅደስ ውስጥ ያለው የጥፋት ርኩሰት፣ ታላቁ መከራ፣ የተፈጥሮ አደጋዎች፣ ለሰው ልጅ የምልክቱ መገለጥ፣ የበለሲቱ ዛፍ ምሳሌ፣ የኢየሱስ ክርስቶስ መምጣቱ ማረጋገጫዎች፣ የኢየሱስ ክርስቶስን መምጣት ተዘጋጅተው ስለመጠበቅ ዝግጅት፣ የባሪያውና የአለቃ ምሳሌ ናቸው ( ማቴ ፳፬፥፩-፶፩)። የክርስቲያኖች ቁጥር እያነሰ መምጣት፣ የአብያተ ክርስቲያናት መዘጋት፣ ሰውን ሰው የሚያሰኘዉን ክብርና ሞገስ ትቶ በግብሩ እንስሳትን ሲመስል፣ የቅድስና ሕይወት ሲጠላና ሲናቅ፤ በአንጻሩ ደግሞ የሰው ልጅ ለረከሰው ለዚህ ዓለም ምኞትና ፈቃድ ሲገዛ ስናይ የዚህ ዓለም ፍጻሜ ጊዜው እየደረሰ መሆኑን ዐውቀን፤ ኖኅ በብዙ ኃጢአተኞች መካከል ቢኖርም ራሱን በቅድስና ጠብቆ እንደኖረ (ዘፍ.፮-፰)፤ ሎጥም እንዲሁ በብዙ ኃጢአተኞች መካከል ሲኖር በእነርሱ ኃጢአት እንዳልተባበረ (ዘፍ. ፲፱) ከዚህ ዓለም ክፉ ሥራ ተለይተን ራሳችንን በቅድስና በመጠበቅ መጋደል አለብን። ዓለሙ ስለ እምነታችን ቢጠላንም እኛም ስለ ክፉ ሥራዉ ንቀነው መኖር የግድ መሆኑን እንወቅ እንጂ ስለ እምነት፣ ስለ ቅድስናም ከዓለም በጎ ነገር መጠበቅ የለብንም። በተለያዩ ሁኔታዎች የሚደርሱብንን ፈተናዎች ሁሉ በትዕግሥት እንቀበላቸዉ እንጂ በማማረር አንዘን፤ ምክንያቱም ስለ ስሜ በዓለም ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ ተብለናልና። በአሁኑ ሰዓት በተለያዩ ቦታዎች፣ ሁኔታዎች ልንሆን እንችላለን። ግን ምን ማድረግ ይገባናል ? ተዘጋጅተን መጠበቅ!

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተለያዩ ወቅቶችና ሀገራት ብዙ ሐሰተኛ ክርስቶሶች እንደሚነሡ ተናግሯል። የጌታችን ቃል ሳይፈጸም አይቀርምና ከዚህ ቀደም ብዙ ሰዎች «እኔ ክርስቶስ ነኝ» በማለት ተነሥተው ነበር። በዮሐንስ ራእይ ላይ ዋናው አውሬ ተብሎ የተጠቀሰውና በቅዱስ ጳውሎስ «የዐመፅ ሰው እርሱም የጥፋት ልጅ» የተባለው ብዙ ጥፋትና መከራ የሚያደርሰው ባለ 666 ዓ.ም (ስድስት ስድሳ ስድስት) መለያ ምልክቱ ሐሰተኛ ክርስቶስ እስኪገለጥ ድረስ ብዙ ሐሰተኞች ክርስቶሶች ተነሥተዋል። በእውነተኛው ንጉሥ ክርስቶስ ዳግም መምጣት የሚደመሰሰው ሐሳዊ መሲሕ የመጨረሻውና ለሦስት ዓመት ከመንፈቅ ቤተ ክርስቲያንን የሚወጋ የታላቁ መከራ ፈጻሚና አስፈጻሚ ይሆናል (ራእ ፲፫፥፭)። ጌታችን እስኪመጣ ድረስ እንዳንሰናከል አስቀድሞ «ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና፤ ብዙዎችንም ያስታሉ፤ … በዚያን ጊዜ ማንም እነሆ፥ ክርስቶስ ከዚህ አለ ወይም ከዚያ አለ ቢላችሁ አትመኑ» ሲል ያስጠነቀቀን ለዚህ ነው።

በሀገራችንም ኢትዮጵያም በአፄ ልብነ ድንግል ዘመነ መንገሥት «እኔ ክርስቶስ ነኝ» የሚል ሐሳዊ (ሐሰተኛ) ክርስቶስ ተነሥቶ እንደነበር በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ተመዝግቧል። ይህ ሐሳዊ ልክ እንደ እውነተኛው ክርስቶስ ፲፪ ሐዋርያት፣ ፸፪ አርድእትና ፴፮ ቅዱሳት አንስትን አስከትሎ ክርስቶስ እንደሆነ በመናገር በየሥፍራው ሲንቀሳቀስ ንጉሡ አስቀርበው «አንተ ማን ነህ?» ቢሉት በድፍረት «እኔ ክርስቶስ ነኝ» አላቸው። ንጉሡም «ክርስቶስማ ከድንግል ማርያም ተወልዶ አስተምሮ፣ ተሰቅሎ፣ ዓለምን አድኖ ከሞት ተንሥቶ ዐርጓል፤ ዳግም ዓለምን ለማሳለፍ ይመጣል፤ አንተ ግን ማነህ?» አሉት፤ እርሱ ግን «አዎ ትክክል ነው። ከዚህ ቀደም ከቤተ እሥራኤል ከምትሆን ከድንግል ማርያም ተወልጄ፣ አስተምሬ፣ ተሰቅየ፣ ሙቼ፣ ተነሥቼ ዐርጌ ነበር፤ አሁን ድግሞ ጥቁሮች አፍሪካውያን ባይታወር አደረገን እንዳይሉኝ ከእናቴ ከድንግል መርዐተ ወንጌል ለጥቁሮቹ ዳግም ተወልጄ ነው» አላቸው። ንጉሡም «ሰይጣን በሰው እያደረ እንዴት ይጫወታል» ብለው በሰይፍ አስቀጡት፤ ተካታዮቹም ተበተኑ ይባላል።

ጌታችን ለሐዋርያቱ ስለ ዳግም ምጽአቱ ብዙ ምልክቶች ነግሯቸዋል። ከምልክቶቹ መካካል አንዱ ጦርነት ነው። ጦርነት ቀደምት የነበረ፣ በአሁኑ ዘመን በብዛት የተከሰተ ነገር ግን በተለይ በዚህ ጊዜ በብዙ ሀገራት፣ በኛ ሀገረ ጭምር እየተካሄድ ነው፡፡ ጦርነት በቀደምት ዘመናት ሴቶችን፣ አቅመ ደካማ ሽማግሌዎችንና ሕፃናትን ለእልቂትና ለጥፋት የማያጋልጥ ነበር። በዚህ ጊዜ ግን ጦርነት ማንንም የማይለይ፣ ለማንም የማይራራ፣ የሁሉን ደም የሚያፈስና እጅግ አስከፊ ሆኗል። ይህንንም ጌታችን የዳግም ምጽአቱን ምልክት ለጠየቁት ለደቀ መዛሙርቱ ሁለተኛ ምልክት አድርጎ «ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፥ አትደንግጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው። ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣልና» ሲል ተናግሯል። (ማቴ.፳፬፥፮)

ሌላውና አሳዛኙ ጉዳይ የፍቅር መቀዝቀዝ ነው፤ ፍቅር የሕግ ፍጻሜ ነውና የሰው ልጅ ፍቅርን ማጣት የለበትም። አሁንም «ከዓመፃም ብዛት የተነሣ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች» የሚለው ትንቢት እንዳይፈጸምብን ፍቅርን መንከባከብ፣ ማልማትና ማስፋት ይገባል። (ማቴ.፳፬፥፲፪)።  ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ነው፤ ፍቅር የመልካምና በጎ ነገር ሁሉ መገኛና ምንጭ ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእርሱ ቤተመቅደስ አድርጎ ሲያከብረን ጠላት ዲያብሎስ ደግሞ ይህንን ቤተመቅደስ ለማፍረስ ሁሌም ሩጫ ላይ ነው፤ ስለዚህም ሁልጊዜም በፍቅር መኖር ይገባናል።

ወንጌል ለዓለም መዳረስ ለደቀ መዛሙርቱ የዳግም ምጽአቱ ምልክቶች ሁነው ከተሰጡት አንዱ ነው። በፍርድ ቀን በክርስቶስ አምኖ እና እምነቱን በሥራ ገልጾ ስለመኖር ሲጠየቅ «አልሰማሁም፤ አላየሁም፤ አላወኩም» የሚል ከኃጥአን ጋር ይፈረድበታል፤ «ለአሕዛብም ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፥ በዚያን ጊዜም መጨረሻው ይመጣል» ተብሎ እንደተነገረው በሁሉም ቤት ወንጌል ይሰበካል፡፡ (ማቴ.፳፬፥፲፪)። በመሆኑም በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽአት ዕለት «ንዑ ኀቤየ ቡሩካኑ ለአቡየ ትረሱ መንግሥተ ሰማያት ዘድልው ለክሙ እምቅድመ ይትፈጠር ዓለም [እናንተ የአባቴ ቡሩካን ኑ፥ ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ውረሱ]» እንድንባል ቅዱስ ቃሉን ሰምተን፣ አምነንና ታምነን እስከ መጨረሻው በሕገ እግዚአብሔር መመራትና በበጎ ምግባር በቅድስና ሕይወት ልንኖር ይገባል፡፡ (ማቴ.፳፭፥፴፬)

የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና ተዘጋጅታችሁ ኑሩ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም እና ለአርዓያነት በተገለጠ ጊዜ አመጣጡ በአጭር ቁመት እና በጠባብ ደረት ተወስኖ በትሕትና ነበር። ዳግመኛ የሚመጣው ግን በግርማ መለኮት በክበበ ትስብዕት ነው።  ስለዚህ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና ተዘጋጅታችሁ ኑሩ ብሎ አስተማረን። ያቺን ቀን ከእርሱ በቀር የሚያውቃት የለም። በኖኅ ዘመን እንደነበረው የእርሱም መምጣት እንደዚያ ይሆናል። ባለቤት ከሌሊቱ በየትኛው ክፍል ሌባ እንደሚመጣ ቢያውቅ ኖሮ በነቃና ቤቱን በጠበቀ ቤቱም ሊቆፈር ባልተወው ነበር። ስለዚህ እናንተ ደግሞ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፤ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና። ይህ ቀን ስለማይታወቅ ሁል ጊዜ በንስሐ እና በሥጋ ወደሙ ተዘጋጅተን ልንኖር ይገባናል። ቅዱስ ጴጥሮስ የጌታችን ምጽአት የሚዘገይ እንዳልሆነ ሲያስረዳ «ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፥ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሣል (፪ኛ ጴጥ ፫፥፱)» ብሏል። እስከመጨረሻው የጸና ይድናልና እስከመጨረሻው ጽኑ። ለመከራ አሳልፈው ሲሰጧችሁ፣ ሲገድሏችሁ፣ ስለ ስሜም የተጠላችሁ ስትሆኑ በእምነታችሁ ጽኑ። ብዙዎች ሲሰናከሉ፣ እርስ በእርሳቸውም አሳልፈው ሲሰጣጡ፣ ከአመጻም ብዛት የተነሳ ፍቅር ስትቀዘቅዝ በእምነታችሁ ጽኑ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም «በጊዜውም ያለጊዜውም ጽና» ያለው ለዚህ ነው (፪ኛ ጢሞ ፬፥፪)። በዚህ ወቅት መከራን መታገስ፣ አስፈላጊም ሆኖ ሲገኝ መሥዋዕትነትን በመክፈል ጽናትን ማረጋገጥ ይገባል። እስከ መጨረሻው በጽድቅ አገልግሎት የሚጸና በጌታ ምጽዓት የክብር ትንሣኤ ይነሣልና።

ከበለስ ምሳሌነት ወስደን እንድንማር ሌላ አስደናቂ ሥነ ፍጥረታዊ ምሳሌ ጌታችን ሰጥቶናል። «ምሳሌውንም ከበለስ ተማሩ፤ ጫፍዋ ሲለሰልስ ቅጠልዋም ሲያቈጠቍጥ፥ ያን ጊዜ በጋ እንደ ቀረበ ታውቃላችሁ» ማቴ. ፳፬፥፴፪። በመጀመርያ የበለስን ነገር መናገር ይገባል። በለስ በክረምት የምትደርቅ በበጋ የምትለመልም ወይም ክረምት ከማይስማማቸው ዕፅዋት አንዷ በመሆኗ ስትለመልም የክረምቱ ጊዜ ማለፉን የበጋ ጊዜ መተካቱን ሰው እሷን ተመልክቶ መረዳት ይችላል። እንደዚህም ሁሉ እናንተም ከላይ የተዘረዘሩት ምልክቶች ሁሉ ሲከሠቱ የመጨረሻው የፍርድ ቀን፣ የዓለም ፍጻሜና የጌታ ዳግም መምጣት ጊዘው እንደቀረበ ዕወቁ። ቅርበቱም የደጃችሁን ያህል እንደሆነ ዕወቁ ብሎ የጊዜ ማወቂያ ምሳሌ አደርጎ ነው የጠቃሳት።

የደብረ ዘይት ዕለት ጻድቃን የሚናፍቋት የተስፋ መንግሥተ ሰማያት ዕለት ናት። ተስፋ ብርሃናዊ መገስገሻ መንገድ ናት። ተስፋ የማይታየውን አጉልታ፣ ሩቁን አቅርባ የምታሳይ መነጽር፣ መከራውን ደስታ የምታደርግ ሐሴት፣ ደካማውን የምታበረታ ኃይል ናት። የሰው ልጅ የተስፋ መንግሥት ሰማያትን ፍጹም ደስታ፣ የቀቢጸ ተስፋ ገሀነመ እሳትን ፍጹም ሥቃይ ቢያውቅ፣ ቢረዳው ኖሮ በዚህ ዓለም ይድላኝ ሳይል ኑሮው በመንኖ ጥሪት ይሆን ነበር። «ወምንተ ይበቁዖ ለሰብእ ለእመ ኲሎ ዓለመ ረብሐ ወነፍሶ ሃጉለ። ወምንተ እምወሀበ ሰብእ ቤዛሀ ለነፍሱ [ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጎድል ምን ይጠቅመዋል? ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል?]» (ማቴ ፲፮፥፳፮ ) እንዲል። ተስፋ የምናደርጋት መንግሥተ ሰማያት የእግዚአብሔር መንግሥት ናት። እርሷም እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያዘጋጃት፣ የእግዚአብሔር ምሕረቱና ጥበቡ የሚገለጽባት፣ በትንሣኤ ዘጉባኤ ፍርድ ቀን በእርሱ ያመኑ የሚገቡባት የእግዚአብሔር ቤት ናት። «በእግዚአብሔር እመኑ፤ በእኔም ደግሞ እመኑ። በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ … እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ ፤ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ።» እንዳል ጌታ ማቴ ፲፬፥፩።

በአጠቃላይ ደብረ ዘይት ሁለት ተቃራኒ ነገሮች የሚፈጽሙበትን የነገረ ዳግም ምጽአት ሁኔታን ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምንማርበት የዐቢይ ጾም ሳምንት ነው። ይኸውም ትንሣኤ ዘለክብር እና ትንሳኤ ዘለሀሳር ነው። አንዱ ከእግዚአብሔር ጋር የሚሆንበት ሌላው ከሰይጣን ጋር ኑሮው የሚወሰንበት፣ አንዱ መንግሥተ ሰማያትን የሚወርስበት ሌላው ገሀነመ እሳት የሚገባበት፣ አንዱ የሚደሰትበት ፣ ሌላው ዋይታ የሚያሰማበት፣ የበረከትና የመርገም ቀን፣ የተስፋና ተስፋ የመቁረጥ ቀን፣ የደስታና የጭንቅ ቀን፣ የእልልታና የዋይታ ቀን፣ አንዱ ሌላውን የማያድንበት፣ እናት ልጄን የማትልበት፣ ልጅ እናቴን የማይልበት፣ ባልና ሚስት የሚለያዩበት፣ጓደኞች ዳግም የማይገናኙበት፣ ኃጥእ ከጻድቅ መተያየት የሚያበቁበት የመጨረሻ እለት ዳግም ምጽአት ናት።

ማጠቃለያ

የእግዚአብሔር ጥሪ ሁሉም የአዳም ዘር መንግሥቱን እንዲወርሱ ቢሆንም የሰይጣንን ወጥመድና አሸከላ ሁሉ አልፈው፤ በሐሰተኞች ምትሐታዊ ተአምራት ሳይሳቡና ሳይሰናከሉ እስከ መጨረሻው ጽንተው በዚያ በዳግመኛ ልደት እና የመጨረሻ የዋጋ ቀን በጌታቸው ቀኝ የሚቁሙ የታደሉ ናቸው። በመንፈሳዊ ሕይወትም ተዘጋጅቶ መኖር ትልቅ ስፍራ የሚሰጠው ጉዳይ ሲሆን የሚከተሉትን ነጥቦችም በውስጡ ይይዛል፦ ድልዋኒክሙ ንበሩ [ተዘጋጅታችሁ ኑሩ] ( ማቴ፳፬፥፵፬)

ሀ. በጽኑ እምነት መኖር፦

ክርስቶስ ወደዚህ ምድር የመጣበት ዋና ዓላማ እኛ በእርሱ ቤዛነት በፍጹም ልባችን አምነን ከኩነኔ እንድን ዘንድ ነው። ለዚህም ነው “እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኵነኔ የለባቸውም” (ሮሜ ፰፥፩) የሚለው። በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት ማለት በእርሱ አምኖ በትክክለኛው መንፈሳዊ ሕይወት መኖር ማለት ነው። እግዚአብሔርን የምናስደስተው በእምነት ስንኖር ነው። እምነት ከሌለን እርሱን ደስ ማሰኘት አንችልም፤ ለዚህም ነው “ያለ እምነትም ደስ ማሰኘት አይቻልም” (ዕብ ፲፩፥፮) ተብሎ በቅዱሱ መጽሐፍ የተጻፈው። ስለሆነም በጽኑ እምነት መኖር ከሁላችንም የሚጠበቅ ነው።

ለ. በንስሐ ሕይወት መመላለስ፦

ሁላችንም በዚች ፈታኝ ዓለም ላይ ስንኖር በማሰብ፣ በመናገርና በማድረግ ኃጢአትን እንሠራለን። እግዚአብሔር ደግሞ በባሕርይው ቅዱስ ስለሆነ ኃጢአትን ይጸየፋል። ስለሆነም ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ለማድረግ ዘወትር በንስሐ ሕይወት በመመላለስ በቅድስና ሕይወት መኖር ያስፈልጋል።  “ነገር ግን እርሱ በብርሃን እንዳለ በብርሃን ብንመላለስ ለእያንዳንዳችን ኅብረት አለን፥ የልጁም የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻናል” (፩ኛዮሐ ፩፥፯) ስለሚል ቃሉ እርሱ መድኃኔዓለም በዕለተ አርብ ባፈሰሰው ደሙ እንዲያነጻን “ዘወትር ጠዋት ማታ ያለማቋረጥ ባፈሰስከው ደምህ ይቅር በለን፤ አንጻን ልንለው” ይገባል።

ሐ. ቅዱስ ሥጋውንና ደሙን መቀበል፦

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውንና ደሙን እንድንቀበል አዞናል። ስለሆነም ሥርዓተ ቅዳሴውን እየተከታተልን ብቻ ወደ ቤታችን መሄድ ሳይሆን ንስሐ በመግባት ቅዱስ ሥጋውንና ደሙን መቀበል ይኖርብናል። “ዘበልዐ ሥጋየ ወሰትየ ደምየ ቦ ሕይወት ዘለዓለም ወአነ አነሥኦ በደኃሪት ዕለት [ሥጋየን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ህይወት አለው፤ እኔም በመጨረሻው እለት አስነሣዋለሁ]” ዮሐ ፮፥፶፬

መ. በፍቅር ሕይወት መመላለስ፦

ፍቅር የእግዚአብሔር ባሕርይ ነው፤ እኛም በፍቅር እንድንኖር አዞናል። ፍቅር በብዙ ሰዎች ዘንድ እየቀዘቀዘች ባለችበት ወቅት በፍቅር መኖር ታላቅ መታደል መሆኑን ተረድተን በፍቅር ልንኖር ይገባል። እግዚአብሔር አምላካችንን በፍጹም ልባችን በመውደድ እንዲሁም አጠገባችን ያለውን ወንድማችንን በመውደድ ፍቅርን በሕይወት ልንኖረው ይገባል። “በፍቅሬ ኑሩ” (ዮሐ ፲፭፥፱) የሚለውን ትእዛዝ ፈጽመን ቢሆን ኖሮ ዛሬ ላይ በሀገራችንም ሆነ በዓለም ላይ የንጹሐን ደም አይፈስም ነበር። ዘወትር በፍቅር ሕይወት በመመላለስ ጥላቻ እንዲወገድ የበኩላችንን ድርሻ ልንወጣ ያስፈልጋል።

ሠ. በተስፋ መኖር፦

በመንፈሳዊው ዓለም በተስፋ መኖር ማለት በተረጋገጠና እውነተኛ በሆነ ተስፋ መኖር ማለት ነው። መንፈሳዊው ተስፋ እንደ ምድራዊው ተስፋ ይሆናል ወይም አይሆንም በሚሉ ሁለት ሃሳቦች የተከፈለ አይደለም። ፈተናዎችና መከራዎች እንኳን አብዝተው ሊያስጨንቁን ቢሞክሩ ” እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ” (ማቴ ፲፩፥፳፰) ብሎ ጌታችን የተናገረውን በማሰብና በመረዳት በእርሱ እርፍ እያልን በተስፋ መኖር ይገባናል። በተስፋ መኖር በምድራዊውና በሚጠፋው ነገር እንዳንወስድ ያደረግናል። በቀኙ ለመቆም እንዲያበቃን የአምላካችን የልዑል እግዚአብሔር ቸርነት የእመቤታችን የርኅርኂተ ኅሊና የድንግል ማርያም አማላጅነት፣የቅዱሳን ሁሉ ረድኤት አይለየን፤ አሜን።

ጸሎት

አቤቱ አምላካችን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ፣ ዳግም በግርማ መለኮት ፣ በክበበ ትስብእት ፣ በይባቤ መላእክት በምትመጣበት ጊዜ የእግዚአብሔር በግ የሆንህ አንተ በመስቀል ላይ መሥዋዕት ስትሆን በኀዘን ዕንባ ስለቆሰለች እናትህ ብለህ ማረን ፣ በእንተ ማርያም መሐረነ ክርስቶስ ፣ ክርስቶስ ሆይ ስለ ድንግል ማርያም ብለህ ይቅር በለን ፣ አስበን ። በመጨረሻም እንዲህ እያልን እንዘምር “ደምረነ ምስለ ኵሎሙ ቅዱሳን ምስለ እለ ገብሩ ፈቃደከ እለ እምዓለም አሥመሩከ/፪/፣ እለ ዐቀቡ በንጽሕ ሥርዓተ ቤትከ ፣ ወእለሰበኩ በሠናይ/፪/ በሠናይ ዜናከ”። አሜን!


ማጣቀሻዎች/References/


በኢ/ኦ/ተ/ቤ/በሰ/ት/ቤቶች/ ማ/መ/ማ/ቅ ሩቅ ምሥራቅ ማእከል ሚዲያ እና ሕዝብ ግንኙነት ክፍል

መጋቢት ፲፬ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም

ቻይና

ሰሙነ ሕማማት (በመ/ር ኃይለ ማርያም ላቀው)

ሰሙነ ሕማማት እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር ስለ ተገለጠበት፣ የመሥዋዕትነት ሥራ የተሠራበት፣ የሰው ልጆች ድኅነት ስለ ተፈጸመበት፣ መድኃኔ ዓለም በመስቀል ተሰቅሎ ለእኛ ቤዛ መኾኑ በስፋት ስለሚነገርበት ‹ቅዱስ ሳምንት› ይባላል፡፡ በተጨማሪም ‹የመጨረሻ ሳምንት› ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም ጌታችን አምላችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በመዋዕለ ሥጋዌው ለፈጸማቸው የቤዛነትና የአርአያነት ተግባራት ፍጻሜ በመኾኑ ነው፡፡

በዚህ ልዩ ሳምንት ካህናትና ምእመናን በነግህ፣ በሠልስት፣ በቀትር፣ በተሰዓትና በሠርክ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጓዝ ስለ ጌታችን ኢየስስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀል የሚያዘክረውን ምዕራፍ ከቅዱሳት መጻሕፍት በማንበብና በመጸለይ ሕማሙንና ሞቱን ይዘክራሉ፤ ቅዱስ ያሬድ በመጨረሻው ሳምንት በየዕለቱ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸመውን ነገረ መስቀል በተመለከተ ያዘጋጀውን መዝሙር ይዘምራሉ፤ አብዝተው ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡

ሰሙነ ሕማማትን ከሌሎች የዐቢይ ጾም ሳምንታት ልዩ የሚያደርገው ሥርዓት አለ፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሥርዓትና ደንብ መሠረት በሰሙነ ሕማማት ከጸሎተ ሐሙስ በስተቀር ቅዳሴ አይቀደስም፤ ስብሐተ ነግህ አይደረስም፤ ጸሎተ ፍትሐት አይጸለይም፤ ጸሎተ አስተስርዮም አይደረግም፡፡ ጥምቀተ ክርስትናም አይፈጸምም፡፡ ከላይ የተዘረዘሩት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶች አስቀድሞ በዕለተ ሆሣዕና ይከናወናሉ፡፡ በተጨማሪም ማንኛውም ክብረ በዓል በዚህ ሳምንት ቢውል ከትንሣኤ በኋላ ይከበራል፡፡ ይህም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የጸና ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓት ነው፡፡

ሕማምና ሞት የማይገባው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእኛን ሕማምና ሞት ለራሱ በማድረግ በዚህ ሳምንት ለእኛ ቤዛ መኾኑ ይነገራል፡፡ ‹‹ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ፡፡ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጠረ፡፡ እርሱ ግን ግፍን አላደረገም፤ ተንኮልም በአፉ አልተገኘበትም፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ኢሳ. ፶፫፥፬-፲፪)፡፡ ምእመናን ክርስቶስ የተቀበለው የእኛን ሕማም መኾኑን በመዘከር፤ ከማንኛውም የሥጋ ሥራ በመታቀብ ዋዛ ፈዛዛ ባለመነጋገር ሰሙነ ሕማማትን ልናከብር ይገባል፡፡ ብድራትን የማያስቀረው አምላካችን እግዚአብሔር መተላለፋችንና በደላችንን በመደምሰስ የመንግሥቱ ወራሽ አድርጎናልና፡፡

ሰሙነ ሕማማት አስከ አራተኛው ምዕተ ዓመት ድረስ ከዐቢይ ጾም ተለይቶ ለብቻው ይከበር ነበር፡፡ በኋላ ግን በባሕረ ሐሳብ ቀመር መሠረት ጾሙም፣ ሕማማቱም፣ ትንሣኤውም ተከታለው እንዲከበሩ ተደረገ፡፡ ምዕራባውያን ከዐርባ ጾም ውስጥ የመጨረሻውን ሳምንት ሰሙነ ሕማማት ያደርጉታል፡፡ የምሥራቃውያን (ኦርየንታል) ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ግን ዐርባውን ጾም ጨርሰን ከኒቆዲሞስ በኋላ ያለውን ተከታዩን አንድ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት አድርገን እናከብራለን፡፡ ከእነዚህ የሕማማት ሳምንት ውስጥ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስቱ ዕለታት (በሰኞ፣ ማክሰኞ እና ረቡዕ) ያከናወናቸው የድኅነት ሥራዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሰኞ
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ኾኖ በዚህ ዓለም ሲመላለስ በሆሣዕና ማግሥት ከቢታንያ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሁለት ነገሮችን አከናውኗል፤ አንደኛ ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፡፡ ሁለተኛ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል (ማቴ. ፳፩፥፲፪-፲፯፤ ማር. ፲፩፥፲፯፤ ሉቃ. ፲፱፥፵፭-፵፮)፡፡ በቅዱስ ማቴዎስ አገላለጥ ‹‹በማግሥቱ ተራበ›› የሚል ቃል እንመለከታለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም›› ይላል (ኢሳ. ፵፮፥፳፭)፡፡ በቅዱስ ወንጌል በመጀመሪያ ቃል እንደ ነበር፤ ያ ቃል ቀዳማዊ እንደ ኾነ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ነበር፤ ያም ቃል እግዚአብሔር እንደ ኾነ ተጽፏል (ዮሐ. ፩፥፩-፪)፡፡ ጌታችንም በመዋዕለ ትምህርቱ ሲያስተምር፡- ‹‹የእኔስ መብል የላከኝን የአባቴን ፈቃድ አደርግ ዘንድ፤ ሥራውንም እንፈጽም ዘንድ ነው፤›› ሲል ተናግሯል (ዮሐ. ፬፥፴፬)፡፡ ታዲያ ጌታችን ለምን ተራበ? ሰማያውያን መላእክት እንዳይራቡ አድርጎ የፈጠረ፤ እስራኤልን ገበሬ በማያርስበት፣ ዘር በሌለበት፣ ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ የመገበ፤ ድኅረ ሥጋዌ በአምስት አንጀራና በሁለት ዓሣ ከአምስት ሺሕ የሚበልጡ ሰዎችን የመገበ ጌታ ‹‹ተራበ›› ተብሎ ሲነገር እጅግ ይደንቃል፡፡ በእርግጥ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው በመኾኑ አልተራበም አንልም፡፡ የጌታችን ረኃብ የድህነት (የማጣት) አይደለም፡፡ የክርስቶስ ረኃቡ የበለስ ፍሬ ሳይኾን የሃይማኖትና የመልካም ሥነ ምግባርን ፍሬ የሻ መኾኑን ለማጠየቅ ‹‹ተራበ›› ተባለ፡፡ ‹‹በለስ ብሂል ቤተ እስራኤል እሙንቱ›› እንዲል፡፡ ጌታችን የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረግሟል፡፡ በአይሁድ ጉባኤ የነገሠውን ኃጢአት፤ በበለስ አንጻር መርገሙን ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ‹‹በአንጻረ በለስ ረገማት ለኃጢአት፤ በበለስ አንጻር ኃጢአትን ረገማት›› ብሏል፡፡

እስራኤልም በአንድ ወገን የተጠበቀባቸውን ፍሬ ባለማፍራታቸው ተረግመዋል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እስራኤል ከፍቅር ይልቅ እርግማን እንዳገኛቸው፤ አሕዛብ ደግሞ የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው ያመኑበትን የእግዚአብሔር የጸጋ ልጁ ለመኾን መብቃታቸውን ሲመሰክር እንዲህ ይላል፤ ‹‹አሕዛብ አስተጋብኡ ጽጌሬዳ በኂሩቱ ወሶኩሰ ተርፈ ኀበ አይሁድ ዘውእቱ ሕፀተ ሃይማኖት፤ አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾኹ ተረፈ፡፡ ይኸውም የሃይማኖት ጉድለት ነው፤›› ብሎ ተርጕሞታል፡፡ እሾኽ የእርግማን፤ አበባ የእግዚአብሔር ጸጋ ልጅነት ምሳሌ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! ዛሬ ጌታችን ወደ መቅደስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይኾን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል ‹‹ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤›› ይለናልና እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገውን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ እናፍራ (ማቴ. ፫፥፰፤ ገላ. ፭፥፳፪)፡፡ ጌታችን በዳግም ልደት ሲመጣ ከሰው ልጅ ሃይማኖት መገኘቱ አጠራጣሪ እንደ ኾነ ተናግሯል፡፡ ‹‹የሰው ልጅ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ሃይማኖት ያገኝ ይኾንን?›› ሕይወታችንን በአምላካዊ ሥልጣኑ የቃኘ አምላክ ለፍርድ በመጣ ጊዜ የእምነት ፍሬ አፍርተን እንዲያገኘንና ዘላለማዊ መንግሥቱን እንዲያወርሰን የጽድቅ ሥራ ለመሥራት እንትጋ፡፡

 

ማክሰኞ
በማቴዎስ ወንጌል ፳፩፥፳፰፤ ፳፭፥፵፮፤ ማርቆስ ወንጌል ፲፪፥፲፪፤ ፲፫፥፴፯፤ በሉቃስ ወንጌል ፳፥፱፤ ፳፩፥፴፰ የሚገኙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ማክሰኞ ዕለት የሚነገሩ ትምህርቶችን ይዘዋል፡፡ በዚህ ዕለት ጌታችን በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ ዕለቱ ‹የትምህርት ቀን› ይባላል፡፡ ክርስቲያን የኾነ ዅሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃይማኖት ትምህርት ሲማር፣ ሲጠይቅ መሰንበቱ መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡

በዚህ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሥልጣኑ ተጠይቋል፡፡ ጠያቂዎቹ የካህናት አለቆችና የሕዝብ አለቆች ሲኾኑ፣ ጥያቄውም፡- ‹‹በማን ሥልጣን እነዚህን ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን የሰጠህ ማነው?›› የሚል ነበር፡፡ ይህ ጥያቄ ጌታችን ሰኞ ዕለት ሁለት ነገሮችን ማከናወኑን ተከትሎ የተነሣ ጥያቄ ነው፡፡ ይኸውም ጌታችን ሲያደርጋቸው የነበሩ ተአምራትና ድንቅ ድንቅ ሥራዎች የካህናት አለቆችን ስላስቀኗቸው ጌታችንን ከሮማ መንግሥት ባለ ሥልጣናት ጋር ለማጋጨት የቀየሱት ስልት ነው፡፡ ጌታችን በቤተ መቅደስ የነበሩትን ነጋዴዎችን አባሯል፤ መደባቸውን ገለባብጧል፡፡ ነጋዴን ማባረርና መደብን ማስለቀቅ መንግሥታዊ ሥራ ነው፡፡ ጌታችን ‹‹በራሴ ሥልጣን›› ቢላቸው ፀረ መንግሥት አቋም አለው በማለት ከሮማ መንግሥት ዘንድ ለማሳጣት ነበር ዕቅዳቸው፡፡

ጌታችን ግን የፈሪሳውያንን ጠማማ አሳብ ስለሚያውቅ ‹‹የዮሐንስ ጥምቀት ከየት ነው? ከሰማይ ነው ወይስ ከምድር?›› ሲል ጠይቋቸዋል፡፡ ጌታችን ፈሪሳውያን ላቀረቡለት ጥያቄ ቀጥተኛ ምላሽ አልሰጠም፡፡ ምክንያቱም ጥያቄው ለከሳሾቹ ዓላማ መሳካት አመቺ ኹኔታን ስለሚፈጥር ጥያቄውን በጥያቄ መልሶላቸዋል፡፡ እነርሱም ‹‹ከሰማይ ነው›› ቢሉት ‹‹ለምን አላመናችሁበትም?›› እንዳይላቸው፤ ‹‹ከሰው ነው›› ቢሉት ደግሞ ሕዝቡ ዮሐንስን እንደ አባት ይፈሩት፣ እንደ መምህር ያከብሩት ነበርና ሕዝቡ እንዳይጣሏቸው ስለፈሩ ‹‹ከወዴት እንደ ኾነ አናውቅም›› ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም ‹‹እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም›› አላቸው፡፡ ይህን ጥያቄ መጠየቃቸውም እርሱ የሚያደርጋቸውን ተግባራት ዅሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተውት አልነበረም፤ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ ነበር እንጂ፡፡

ዛሬም ቢኾን መልካም ሥራን በሠራን ጊዜ ከልዩ ልዩ ወገኖች የሚመጡ ፈተናዎች ለመልካም ሥራችን እንቅፋት ሊኾኑ እንደሚችሉ መገንዘብ አለብን፡፡ ብዙ ወገኖች ‹‹ለቅን አሳባችን ለምን ሰዎች ክፉ ነገር ይመልሱልናል?›› በማለት ሲጠይቁ ይሰማል፡፡ ለቅን አሳባችን ከዓለም ዘንድ ተቃራኒ ነገር እንደሚጠብቀን ለመረዳት ‹‹ዓለም የሚወደው የገዛ ወገኑን ነው›› የሚለውን የጌታችንን ትምህርት ልብ ይሏል፡፡ በዘመናችን አሳልፈው ሊሰጡን የሚፈልጉ ሰዎች ፈታኝ ጥያቄ እንደሚያቀርቡልንም ከወዲሁ ልንገነዘብ ይገባል፡፡

ረቡዕ
በቅዱስ ማቴዎስና በቅዱስ ማርቆስ አመዘጋገብ መሠረት በዕለተ ረቡዕ የሚከተሉት ሦስት ነገሮች ተፈጽመዋል፤
• አንደኛ የካህናት አለቆች፣ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ ተማክረዋል፤
• ሁለተኛ ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ አንዲት የተጸጸተች ሴት ሽቱ ቀብታዋለች፡፡
• ሦስተኛ ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያንና ከካህናት አለቆች ዘንድ ሠላሳ ብር ለመቀበል ተስማምቷል፡፡

የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሹማምት በጌታችን ላይ ይሙት በቃ ለመወሰን የሰበሰቡት ሸንጐ ‹ሲኒሃ ድርየም› ይባላል፡፡ በዚህ ሸንጐ ላይ በአብዛኛው የተሰየሙት ሰዱቃውያን ሲኾኑ ሌሎቹ ደግሞ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ነበሩ፡፡ ሸንጐው በአጠቃላይ ሰባ ሁለት አባላት የነበሩት ሲኾን የሚመራውም በሊቀ ካህናቱ በቀያፋ ነበር፡፡ በዕለቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት ይዘው እንደሚገድሉት አይሁድ በዚህ ሸንጎ መክረዋል፡፡ ከዳተኛው ይሁዳም ጸሐፍት ፈሪሳውያንና የካህናት አለቆች በጌታን ላይ የነበራቸውን ጥላቻ ያውቅ ስለነበር ‹‹ምን ልትሰጡኝ ትወዳላችሁ? እኔም አሳልፌ እሰጣችኋለሁ፤›› በማለት ጌታችን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ተስማቷል፡፡

ጌታችን ያስተምር በነበረበት ወቅት የአስቆሮቱ ይሁዳ ከምእመናን ለሚገባው ገንዘብ ሰብሳቢ (ዐቃቤ ንዋይ) ነበር፡፡ ከሚሰበሰበው ሙዳየ ምጽዋት ለግል ጥቅሙ እየቀረጠ የማስቀረት የእጅ አመል ነበረበት፡፡ ይሁዳ ፍቅረ ንዋይ እንደሚያጠቃው ድብቅ አመሉ ጎልቶ የወጣው ጌታችን በለምጻሙ በስምዖን ቤት ሳለ አንዲት ሴት ዋጋው ውድ የኾነ ሽቱ በቀባችው ጊዜ ነው፡፡ በዚያች ዕለት ይሁዳ የተቃውሞ ድምፅ ካሰሙት አንዱ ነበር፡፡

‹‹ይህ ሽቱ ተሽጦ ለድሆች ቢሰጥ መልካም ነበር፤›› በማለት ያቀረበው አሳብ ‹‹አዛኝ መሳይ ቅቤ አንጓች›› እንደሚባለው ነበር፡፡ ሽቱ ሲሸጥ የሚያገኘው ጥቅም አለ፤ ሽቶው በጌታችን እግር ሥር ከፈሰሰ ለእርሱ የሚተርፈው የለም፡፡ ይሁዳ ተቆርቋሪ መስሎ ያቀረበው አሳብ ተቀባይነት በማጣቱም ማኩረፊያ ያገኘ መስሎት በቀጥታ ከካህናት አለቆች ዘንድ ሔዶ ጌታንን በሠላሳ ብር ለመሸጥ ተዋዋለ፡፡ ይህ ታሪክም በሦስቱ ወንጌላት ውስጥ በሚከተሉት ምዕራፎች ተመዝግቦ እናገኛዋለን፤ ማቴ. ፳፮፥፫-፲፮፤ ማር. ፲፬፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፪፥፩፮፡፡

የአስቆሮቱ ይሁዳ እንደ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ተምሯል፡፡ በረከተ ኅብስቱን ተመግቧል፡፡ ልዩ ልዩ ተአምራት በጌታችን እጅ ሲደረጉ ዅሉ ተመልክቷል፡፡ ጌታችንም ከሌሎች ሐዋርያት ሳይለየው እግሩን አጥቦታል፡፡ ከዳተኛው ይሁዳ ግን ለሐዋርያነት የጠራውን፣ ተንበርክኮ እግሩን ያጠበውን ጌታ ለሞት አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ ‹‹የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሔዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት!›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፳፮፥፳፬)፡፡ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ዘንድ ፍቅሩን ገንዘብ ሲያደርጉ ይሁዳ ግን እርግማንን ነው ያተረፈው፡፡ ‹‹ገንዘብ የኃጢአት ሥር ነው፤›› ተብሎ አንደ ተነገረ የኃጢአት ሥር የተባለው ገንዘብ የክርስቲያኖችን ሕይወት ያዳክማልና ምእመናን እንደ ይሁዳ በገንዘብ ፍቅር እንዳንወድቅ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ሰው ‹‹ይህን ዓለም ቢያተርፍ ነፍሱን ከጐዳ ምን ይጠቅመዋል?›› ተብሎ የተነገረውን ቃል ልብ ማለት ጠቃሚ ነው፡፡
ክርስቲያን ነን በማለት የክርስትናውን ስም በመያዝ እምነታቸውን፣ የቆሙበትን ዓላማ በመገንዘብ የሚለውጡ ሰዎች ዛሬም እንደ ይሁዳ ጌታችንን እየሸጡት እንደ ኾነ ሊገነዘቡት ይገባል፡፡ ለድሆች መመጽወት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ዳሩ ግን በድሆች ስም የሰውን ገንዘብ ለግል ጥቅም ማዋል እጅግ የከፋ ኃጢአት ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለገንዘብ ብለው ድሆችን ለረኃብ ለችግር ባልንጀራቸውን ለመከራ እና ለሞት አሳልፈው ሲሰጡ ምንም አይጸጽታቸውም፡፡ እውነተኛ ክርስቲያኖች ግን ሕይወታችንን ለገንዘብ ፍቅር ሳይኾን ለእምነታችንና ለባልንጀራችን አሳልፈን መስጠት ይኖርብናል፡፡ በፍቅረ ንዋይ ተጠምደን ሰዎችን አሳልፎ በመስጠት ለአይሁዳዊ ሸንጐ ምቹ ኾነን መገኘት እንደሌለብን መገንዘብ አለብን፡፡

ይቀጥላል …

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡– ስምዐ ተዋሕዶ (ልዩ ዕትም ዘሰሙነ ሕማማት)፣ ከሚያዝያ ፩ -፲፭ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም፣ ገጽ ፬-፮፤ ማኅበረ ቅዱሳን፣ አዲስ አበባ፡፡

ሆሳዕና 🌿🌿🌿

(በመምህር ኃይለ ማርያም ላቀው)

ሆሳዕና የሚለው ቃል በዕብራይስጥ ሆሼዕናህ የሚል ሲሆን ትርጉሙም እባክህ አሁን አድን ማለት ነው፡፡ አቤቱ እባክህ አሁን አድን፣ አቤቱ እባክህ አሁን አቅና፣ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩከ ነው (መዝ.117፡25-26)። የሆሳዕና በዓል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ የሚቀድሙትና የሚከተሉት ሕዝብ በተለይም አእሩግና ሕፃናት ሆሳዕና ለዳዊት ልጅ፣ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፣ ሆሳዕና በአርያም በማለት ጌታችንን በክብር መቀበላቸው የሚታወስበት በዓል ነው፡፡ በዓሉም ሆሳዕና የሚለውን ስያሜ ያገኘው በዕለቱ ከተዘመረው መዝሙር ነው፡፡

በሌላ አነጋገር ይህ ዕለት የጸበርት እሑድ/ Palm Sunday/ ይባላል፡፡ ታሪካዊ አመጣጡ የመልካም ምኞትና የድል አድራጊነት መገለጫ ሆኖ ከደገኛው አባታችን ይስሐቅ ልደት ጋር ተያይዞ የመጣ ነው፡፡ ይኸውም ሣራ የወላድነት ዕድሜዋን ጨርሳ ልማደ እንስት ከተቋረጠባት በኋላ ሁሉን ቻይ የሆነ አምላክ ይስሐቅን በሰጣት ጊዜ ዘመዶችዋ የተሰማቸውን ደስታ ለመግለጽ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ የጎበኛትን አምላክ አመስግነዋል፡፡ እስራኤል ከአስከፊው የግብፃውያን አገዛዝ ተላቀው ባሕረ ኤርትራን በደረቅ ሲሻገሩ የተሰማቸውን እጥፍ ድርብ ደስታ በገለጡ ጊዜ፣ እንዲሁም ዮዲት የተባለች ንግሥተ እስራኤል ሆሎፎርኒስ የተባለ አላዊ ንጉሥን ድል ባደረገች ጊዜ ቤተ እስራኤል እንደ ሰንደቅ ዓለማ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ አደባባይ ወጥተው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡

በዘመነ ሐዲስም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር ከዲያብሎስ ቁራኝነት ከሲኦል ባርነት ነጻ ለማውጣት ወደ ዙፋን መስቀሉ /ሉቃ.22፤18/ በተጓዘ ጊዜ ሕፃናት እና አእሩግ ነጻ የሚወጡበት ቀን መድረሱን እነርሱ ሳያውቁ እግዚአብሔር ባወቀ ዘንባባ በመያዝ ዘምረዋል፡፡ እስራኤል ዘንባባ በመያዝ እንዳመሰገኑት እኛም እስራኤል ዘነፍስ ዕለቱን ዘንባባ በግንባራችን በማሰር በዓሉን በየዓመቱ እያስታወስን እናከብራለን፡፡ በዚህ ዕለት ዘንባባ እየተባረከ ለሕዝቡ ይታደላል፡፡

ሕፃናትና አእሩግ “ለዳዊት ልጅ መድኃኒት መባል ይገባዋል” እያሉ ዘምረዋል፡፡ ይህ ሁሉ በአንድ ወገን የነበረው የአቀባበል ሥነ ሥርዓት ሲሆን በሌላ በኩል የነበረው አቀባበል ደግሞ እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ሥርዓተ ኦሪትን፣ ትንቢተ ነቢያትን በሚገባ እንከተላለን ይሉ የነበሩ ጸሐፍት ፈሪሳውያን መምህር ሆይ ደቀ መዛሙርትህን ገሥጻቸው አሉት፡፡ ጌታችንም መልሶ እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ ሲል መልሶላቸዋል፡፡ ቅናት አቅላቸውን ያሳታቸው ፈሪሳውያንም የዋህ የሆነው ሕዝብ ምስጋና ወደ ጥላቻ እንዲለወጥ አድርገዋል፡፡ ከሁሉ የሚያሳዝነው በዕለተ ሆሳዕና እሑድ ዘንባባ ይዘው የዘመሩለትን ጌታ ዓርብ ይሰቀል ዘንድ ይገባል ብለዋል፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ፡፡ በዚህም በነቢዩ ዘካርያስ እንዲህ ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ፡፡ እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም፣ በአህያዪቱ ግልገል በውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል (ዘካ.9፡9፤ ማቴ.21፡4፤ ማር.11፡1-10፤ ሉቃ.19፡28-40፤ ዮሐ.12፤15)፡፡ ጌታችን በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱ የሰላም ንጉሥ መሆኑን ያመለክታል፡፡ እስራኤል ዘመነ ምሕረት ሲሆንላቸው አባቶቻቸው በአህያ ጀርባ ተቀምጠው ይታዩ ነበር፡፡ ጌታም እውነተኛ የኅሊና ሰላም ይዤላችሁ መጣሁ ሲለን በአህያ ጀርባ ወደ ቤተ መቅደስ ሕይወታችን ተጉዟል፡፡

መላእክት በዕለተ ልደቱ በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይገባዋል በምድር ሰላም ለሰው ሁሉ ይሁን/ሉቃ.2፡13/ እያሉ የዘመሩለት የሰላም ባለቤት ነው፡፡ በመዋዕለ ትምህርቱም ሰላሜን እሰጣችኋለሁ/ዮሐ.14፡27/ ብሎ እንዳስተማረ ያን ሰላም የሚሰጥበትን ዕለት መቅረቡን ለማመልከት ነው፡፡ በሌላ በኩልም በአህያ ጀርባ መቀመጡ ኅቡዕ ምሥጢር አለው፡ በአህያ ጀርባ የተቀመጠ ሰው ሌላውን አሳድዶ አይዝም፣ እርሱም ሮጦ አያመልጥም፡፡ በዚህም ጌታችን በእምነት ለሚፈልጉት የሚገኝ ቅርብ ሲሆን በእምነት ለማይፈልጉት ግን የማይገኝ መሆኑን አስተምሯል፡፡ ስለዚህ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ፀሐይ ዕድሜያችን ሳትጠልቅ በእምነት እንፈልገው፡፡ የአህያን ጀርባ ያልናቀ ጌታችን ትሑት ሰብእና እና የተሰበረ ልቡና ወዳለው ሰው ዘወትር ይጓዛል፣ የተዋረደውንና የተሰበረውን ልብ አይንቅም (ኢሳ.66፡2፤ መዝ.50፡17)፡፡ በሰሙነ ሕማማት ጸሎተ ፍትሃት ጸሎተ አስተስርዮ ስለማይፈጸም ጸሎተ ፍትሃትና አስተስርዮ የሚደረገው በዚሁ ዕለት ነው።

በሆሣዕና ዕለት ዘንባባ በእጃችን እንደ ቀለበት ማሰራችን የምን ምሳሌ ነው?
✍️ጌታ ለአዳም የሰጠው ቃል ኪዳን ለማስታወስ፦ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድነሃለሁ ያለውን የተስፋ ቃል ለማስታወስ፡፡
✍️ጌታ ለእመቤታችን የገባላትን ቃል ኪዳን ተምሳሌት ነው።
✍️ጌታ ለእስራኤላውያን የሰጣቸው ቃል ኪዳን ተምሳሌት ነው።
✍️ ጌታ አዳምን ከሰይጣን ግዛት ነጻ እንዳወጣው ሁሉ እኛም ከሰይጣን ግዛት፣ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ፣ ከክፋት፣ ከኃጢአት አውጣን ማረን ለንስኃ ሞት አብቃን ከቤትህ አትለየን እንደ ቸርነትህ ይቅር በለን ስንል ለጌታ ዳግም ላናጠፋ ቃል የምንገባበት ነው፡፡

ጌታችን በዕለተ ሆሳዕና ለምን በፈረስ ወይም በበቅሎ ላይ አልተቀመጠም?
ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ “አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፥ እጅግ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፥ እልል በዪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም፥ በአህያይቱ ግልገል በውርጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል”(ትንቢተ ዘካርያስ 9:9)።

በአህያ መቀመጡ፦ ትሕትናን ለማስተማር፣ የሰላም ዘመን ነው ሲል፣ ለፈለጉኝ ሁሉ የቅርብ አምላክ ነኝ ሲል፣ በንጽሕና በየዋህነት ለሚኖሩ ምዕመናን አድሬባቸው እኖራለሁ ሲል፡፡አህያዎች ትሑታን ናቸው ረጋ ብለው ነው የሚሄዱት፤ በቀላሉ ትወጣበታለህ፤ በቀላሉ ትይዘዋለህ፤ እንደፈለክም ታዝዋለህ፤ ጌታችን እኔም ትሑት ነኝ ሲል ነው።

ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ዘንባባ የመነጠፉ ምሥጢር የምን ምሳሌ ነው?
አብርሃም ይሐስቅ በተወለደ ጊዜ ደስ ብሎት ዘንባባ ይዞ እግዚአብሔርን አመስግኗል፡፡ ዘንባባ ደርቆ እንደገና ሕይወት ይዘራል። የደረቀ የምታለመልም አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡ ዘንባባ የሰላም ምልክት ነው፡- የሰላም አምላክ ነህ ሲሉ ነው። ዘንባባ የደስታ መግለጫ ነው፡- አንተ ደስ የምታሰኝ ኃዘናችንንም የምታርቅልን አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡ ዘንባባ እሾሃማ ነው፡- አንተ ሕያው አሸናፊ አምላክ ነህ ሲሉ ነው፡፡ ዘንባባ እሳት አይበላውም ለብልቦ ይተወዋል እንጂ፡፡ ጌታም አንተ ባሕርይህ የማይመረመር ነው ሲሉ ነው፡፡

ሕዝቡ ልብሳቸውን ማንጠፋቸው ለክብሩ መግለጫ ነው፡፡ ልብስ አይቆርቁርም ጌታ የማትቆረቁር ሕግ ሠራሁላችሁ ሲል፡፡ ሌሎችም ሦስት አይነት ቅጠል አነጠፉለት፦ የዘንባባ ዛፍ፣ የቴመር ዛፍ እና የወይራ ዛፍ ቅጠል፡፡ የዘንባባ ዛፍ፦ እሾሀማ ነው። ትእምርተ ኃይል፣ ትእምርተ መዊዕ አለህ ሲሉ ነው፡፡ የቴምር ዛፍ፦ ቴምር ልዑል ነው። ልዑለ ባሕርይ ነህ ሲሉ፤ ፍሬው አንድ ነው – ዋህደ ባሕርይ ነህ ሲሉ፤ ፍሬው በእሾህ የተከበበ ነው – ባሕርይህ አይመመረመርም ሲሉ፡፡ የወይራ ዛፍ ጽኑዕ ነው – ጽኑዓ ባሕርይ ነህ ሲሉ፡፡ ብሩህ ነው ብሩሃ ባሕርይ ነህ ሲሉ፡፡ ዘይት መሥዋዕት ይሆናል – አንተም መሥዋዕት ትሆናለህ ሲሉ፡፡

ታላቋ አህያ በምን ትመሳለለች? ውርንጭላዋስ? ታላቋ አህያ የኦሪት ምሳሌ ናት፡፡ ታላቋ አህያ ሸክም የለመደች ናት፤ ሕገ ኦሪትም የተለመደች ሕግ ናትና፡፡ የእስራኤል ምሳሌ ነው፤ ታላቋ አህያ ሸክም እንደለመደች ሁሉ እስራኤልም ሕግ ለመፈጸም በሕግ ለመራመድ የለመዱ ናቸው፡፡ የአዳም ምሳሌ ነው፡- አዳም ሸክም የበዛበት ነበርና፡፡ የፍጹማን ምሳሌ ናት፡፡ ውርጭላዋ በሕገ ወንጌል ትመሰላለች። ምክንያቱም ወንጌል ኢየሱስ ክርስቶስ የመሰረታት የሠራት አዲሷ ህግ ናትና። በአሕዛብ ትመሰላለች፡- ትንሿ አህያ ሸክም የለመደች አይደለችም እንዲሁም አሕዛብም ሕግን ለመቀበል የለመዱ አይደሉም፡፡ ለሕግ አዲስ ናቸውና፡፡ የእመቤታችን ምሳሌ ናት፡- የዓለም ሸክም አቅላለችና በእመቤታችን ትመሰለላለች፡፡ እመቤታችን ድኅነተ ምክንያታችን ጌታን የተሸከመች ንጽሕት እንከን የሌላት እናት ናትና፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙ ያልታሰሩ አህዮች እያሉ ለምን የታሰሩትን መረጠ? አህዮቹ የታሰሩት ሌባ ሰርቆ ነው ያሰራቸው፡፡ ወንበዴ ሰርቆ ነው ያሰራቸው። አህዮቹ ለጌታ ውለታ ሰርተዋል፡፡ ጌታ ሲወለድ አሙቀውታልና ለጌታ ውለታ ልንመልስ ያልቻልንው እኛ ሰዎች ብቻ ነን፡፡ የታሰሩት እዲፈቱ የመረጠበት ምሥጢር፡-እኔ ከኃጢአታችሁ ልፈታችሁ የመጣሁ ነኝ ሲል ነው፡፡ ወንበዴው አህዮቹን ሰርቆ በመንደር እንዳሰራቸው ዲያብሎስም የሰው ልጆችን በኃጢአት ሰንሰለት ከሲኦል መንደር አስሯቸው ነበርና፡፡ ሐዋርያቱ ሲልካቸው ምን ታደርጋላችሁ የሚላችሁ ሰው ቢኖር ጌታቸው ይሻቸዋል በሏቸው አላቸው በተፈጥሮ ጌታቸው ነውና፡፡ ለታሰሩት መፈታትን ሊሰብክ ሰው የሆነ ጌታችን ከማሰሪያዋ በተፈታች አህያ እንደተቀመጠ ሁሉ ከኃጢአት እስራት በተፈታ ሕይወት ዛሬም ያድራል፤ የኅሊና ሰላምን ይሰጣል፡፡ ስለዚህ ንስሐ ገብተን ጌታችንን ሆሳዕና በአርያም እያልን ልናመሰግነው ይገባል፡፡

ምንጭ፦ ሐመር ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፣ መጋቢት/ሚያዝያ 1996 ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን የሩቅ ምሥራቅ ማእከል አባላት ዕለተ አኮቴትን (የምስጋና ቀን) አከበሩ

በሀገር ውስጥና በውጪ ባሉ የማኅበረ ቅዱሳን ሁሉም መዋቅሮች የሚከበረው ዕለተ አኮቴት (የምስጋና ቀን) በሩቅ ምሥራቅ ማእከል ተከብሯል፡፡ ዕለተ አኮቴት በየዓመቱ ከሆሳዕና በዓል ቀድሞ በሚውለው ዕለተ ዐርብ የሚከበር ሲሆን መርሐግብሩ ማኅበሩ በሚያከናውናቸው አገልግሎቶች ውጤታማ እንዲሆን የረዳውን እግዚአብሔርን የሚያመሰግንበት ነው፡፡ መርሐግብሩ በሩቅ ምሥራቅ ማእከል ስር ባሉ የተለያዩ ሀገራት የሚገኙ ወንድሞችና እህቶች በኦንላይን በተገኙበት የተከናወነ ሲሆን በአባቶች ጸሎት ከተጀመረ በኋላ በቀሲስ ሙሉቀን ብርሃኑ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡ ያሬዳዊ ዝማሬዎች ቀርበዋል፡፡ በአገልግሎታቸው አርኣያ ለሆኑ ወንድሞች እና እህቶች የምስጋና መርሐግብር በማእከሉ ሰብሳቢ ዲ/ን አያናው ፀጋ መሪነት የተከናወነ ሲሆን የበለጠ እንዲያገለግሉ አደራ ጭምር የተሰጠበት ነው፡፡ የሩቅ ምሥራቅ ማእከል ፀሀፊ ዲ/ን ፋንታሁን ትኩ የማኅበሩን መልእከት ያስተላለፉ ሲሆን የቤተ ክርስቲያናችን መከራ በየዘመኑ መልኩን እየቀያየረ መጠኑን እያሰፋ እንደመጣ ገልጸዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አካል የሆነው ማኅበረ ቅዱሳን ባለፉት ፴፪ ዓመታት በእግዚአብሔር አጋዥነት በአውሎና በወጀብ ውስጥ አልፎ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎት እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸው ለዚህም አምላካችንን እግዚአብሔርን ልናመሰግን፤ ለቀጣዩ ደግሞ በጸሎትና በአገልግሎት ተግተን በፍቅርና በእንድነት ተባብረን የበለጠ በመሥራት የቤተክርስቲያንን ችግር ለመቅረፍ ሁላችንም በቁርጠኝነት እንድንዘጋጅ አሳስበዋል።

የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሙተዋልና÷ ተነሥተህ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ። ማቴ. 2÷20

ኅዳር ፮ በዚህች ዕለት ክብርት እመቤታችን ከተወደደ ልጇ ጋር ከስደት በሚመለሱበት ጊዜ ደብረ ቁስቋም ገብተው ካገኛቸው ድካም ያረፉበት ነው። ይህ የቍስቋም ተራራ በግብጽ ከሚገኙ ተራራዎች አንዱ ሆኖ እመቤታችን በሚጠቷ (ከስደት በምትመለስ ጊዜ) ከተወደደ ልጇና ከቅዱስ ዮሴፍና ቅድስት ሰሎሜ ጋር ያረፈችበት ቦታ ነው።

መዘምር ወመተርጕም ቅዱስ ያሬድ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከእናቱ ከእግዝእትነ ማርያም ጋር በዚህ ቦታ ላይ ማረፉንና የቦታውን ታላቅነት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ይናገራል። ቅዱስ ያሬድ ስለቦታው ታላቅነት ሲናገር <<ይቤ ቴዎፍሎስ ሊቀ ጳጳሳት ሶበ ቦዕኩ ውስተ ዝንቱ ቤት አዕረፈት ነፍስየ እምጻማ ዘረከበኒ በፍኖት ኀበ ኃደረት ቅድስት ድንግል ምስለ ፍቁር ወልዳ ኢየሱስ ክርስቶስ : የጳጳሳት አለቃ ቴዎፍሎስ ቅድስት ድንግል ከተወደደ ልጇ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወዳረፈችበት ወደዚህ ቦታ በገባሁ ጊዜ በመንገድ ካገኘኝ ድካም ሰውነቴ አረፈች አለ>> ይልና <<መንግሥቱ ሰፋኒት ዘእምቅድመ ዓለም ወልደ ቅድስት ማርያም ኃሠሠ ምዕራፈ ከመ ድኩም ንጉሥ ዘለዓለም ግሩም እምግሩማን ብርሃነ ሕይወት ዘኢይጸልም ኃደረ ደብረ ቍስቋም ኃይል ወጽንዕ ዘእምአርያም : ዓለም ሳይፈጠር በመንግሥቱ ያለ በንግሥናው የነበረ (መዝ.፸፫÷፲፫) ቅድስት የምትሆን የማርያም ልጅ እንደ ደካማ ማረፊያን ፈለገ (ማረፍን የሚሻ ሥጋን ለብሷልና) ፍጥረታቸው ግሩም ከሆነ ከቅዱሳን መላእክት እጅግ የረቀቀ ግሩም : የማይጨልም ብርሃኑ ዘለዓለማዊ የሆነ የሕይወት ብርሃን(ዮሐ. ፩÷፱) በአርያም ላሉ ለሰማያውያን መላእክት ሁሉ ኃይላቸው ብርታታቸው የሆነ እርሱ በቍስቋም ተራራ ላይ አደረ>> በማለት እርሱ የመላእክት ንጉሣቸው (ሃይ. አበ ዘሄሬኔዎስ ምዕ. ፯÷፯) የሆነ በዚህ ተራራ ላይ ራሱን ዝቅ አድርጎ በትሕትና መገለጡን ይመሰክራል።

ይህች ዕለት ቅዱሳን መላእክት በቍስቋም ተራራ ላይ ክንፋቸውን በእመቤታችንና በተወደደ ልጇ ላይ የዘረጉበትና በሰማይ ምስጋና በምድርም ሰላም ይሁን እያሉ የዘመሩባት ናት።

ዳግመኛም በኋለኛው ዘመን ጌታችን በዚህ በደብረ ቍስቋም ቅዱሳን ሐዋርያቶቹን ሰበሰባቸውና ታቦትንና ቤተ ክርስቲያንን አክብሮ የቍርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለወገኖቹ ሰጣቸው፡፡ ለዚህም ነገር የእስክንድርያ አገር ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱሳን አባቶቻችን ቄርሎስና ቴዎፍሎስ ምስክሮቹ ሆኑ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን። እኛንም በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን። በረከቷም ከሁላችን ጋር ይኑር። ለዘለዓለሙ አሜን።

ምንጭ፦ ስንክሳር ዘኅዳር ፮፣ ዝክረ ቃል ዘቅዱስ ያሬድ (ዘቍስቋም)

እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ጥንተ ስቅለቱ መታሰቢያ በዓል አደረሳችኹ።

ጥቅምት ሃያ ሰባት በዚህች ዕለት የአምላካችን የመድኃኔዓለም የስቅለቱ መታሰቢያ ነው። መድኃኒታችን ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና በቸርነቱ ስለኹላችን ድኅነት ሲል ራሱን ወድዶ ፈቅዶ ለሞት አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ፍቅሩን አሳይቶናል። በቅዱስ ወንጌልም እርሱም መድኃኒታችን “ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም” ብሎ ነግሮናል። እውነት ነው፣ ራስን አሳልፎ ከመስጠት በላይ ምን ድንቅ ነገርና ምን ድንቅ ፍቅር አለ?

ቸሩ አምላካችንን የአስቆሮቱ ይሁዳ ሊያስይዘው የሊቃነ ካህናቱን አገልጋዮች እየመራ አመጣቸው። እነርሱንም ማንን ትፈልጋላችሁ ሲላቸው የናዝሬቱ ኢየሱስን አሉት፣ እኔ ነኝ ቢላቸው የቸሩን አምላክ ድምጽ ሰምቶ አይደለም መቆም በሕይወት መጽናት የሚቻለው የለምና ወደ ኋላቸው ተስፈንጥረው ወደቁ። ደጋግሞም እንዲህ ኾነ። በኋላ ይሁዳ ስሞ አሳልፎ ሰጣቸው።

ከያዙት በኋላ እያዳፉና እየጎተቱ በሰንሰለት አስረው ወደ ቀያፋና ሐና ግቢ ወሰዱት፣ እስከ ሦስት ሰዓትም አላሳረፉትም ሲያሰቃዩት አድረዋል፣ በራሱም ላይ ሰባ ሦስት ስቊረት ያለው ወደ ሦስት መቶ እሾኾችን የያዘ የእሾህ አክሊል ጎንጉነው ቢያደርጉበት የራስ ቅሉን ቀዶ ገብቶ እስከ ልቡ ዘልቋል። እንደምን ጭንቅ ነው? እንዲህም አድርገው ደግሞ እያፌዙ ርኲስ ምራቃቸውን ይተፉበትና በዘንግም ደጋግመው ይመቱት ነበር። እየተፈራረቁ ያለ ምንም ርኅራኄ ቸሩን አምላክ ሥጋው እየተቆረጠ እስኪወድቅ ድረስ ስድስት ሺህ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ጽኑዕ ግርፋትን ገርፈውታል። የገረፉበትም ጅራፍ በላዩ ላይ ሥጋን እየጎመደ የሚጥል፣ ሕመሙ አንጀት ሰርሥሮ የሚገባ ስለት የተያያዘበት ነበር።

በኋላም አላሳረፉትም እንዲህ አድርገውትም በሊቶስጥራ አደባባይ ያንን ዕርጥብ መስቀል አሸክመው ወደ ቀራንዮ ወሰዱት። እርሱ ግን ይህን ኹሉ ግፍ ሲያደርሱበት አንድም አልተናገረም ነበር። በቀራንዮም በአምስት ጽኑዕ ቅንዋት (ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ እና ሮዳስ) ቸንክረው ዕርቃኑን ሰቀሉት።

በዚህች ቀን ድንግል ማርያም ልቧ በሐዘን ተሰበረ መጽናናትንም አልፈለገች ነበር፤ ወዳጁ ቅዱስ ዮሐንስም ፍፁም ለቅሶን አለቀሰ እናቱንም እናት ትሆነው ዘንድ በእግረ መስቀሉ አደራን ተቀበለ። ቅዱሳት አንስት በፍጹም ሀዘንና በዋይታ ዋሉ። በስልጣኑም ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለየ። ሰባት ድንቅ የኾኑ ተአምራትንም አድርጎ አምላክ መኾኑን ገለጠ። ይህም ጽኑዕ የኾነ ለሰማይ ለምድር የከበደ ነገር ሲከሰት ፀሐይ አምላኬን ዕርቃኑ እንዴት አያለሁ ብላ ጨለመች። ጨረቃ ደም ኾነች፣ ከዋክብቱም ረገፉ፣ ንዑዳን ክቡራን ንጹሐን መላእክትም ትዕግስቱን እያደነቁ በጽኑዕ ሐዘንና መደነቅ ከዕፀ መስቀሉ ፊት እንደሻሽ ተነጠፉ።

አስራ አንድ ሰዓት በሆነም ጊዜ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከታላቅ ክብርና ሐዘን ጋር ቅድስት ሥጋውን ከመስቀሉ አውርደው በክብር ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት። በሦስተኛውም ቀን እንደተናገረ ተነሳ።

በዛሬዋ ቀን ቤተ ክርስቲያን የመድኃኔዓለምን የስቅለት በዓል በደማቁ ታከብራለች፤ ይህም የለውጥ በዓል ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰው ስጋውን የቆረሰው መጋቢት 27 ቀን ነው። ይህ በዓል ግን በዐቢይ ጾም ስለሚውል በዐቢይ ጾም ሀዘን እንጂ ደስታ ስለሌለና በዓል ማክበር ስለማይፈቀድ፤ ወደ ጥቅምት 27 ተዛውሮ ደስ ብሎን እንድናከብረው ቤተ ክርስቲያን ስርዓት ሰርታልናለች።

እንዲሁም ይች ዕለት የጻድቁ አባ መብዓ ጽዮን የቃልኪዳን ቀን፣ የማህሌተ ጽጌ ደራሲው አባ ጽጌ ድንግል የእረፍታቸው መታሰቢያ ናት።

ምንጭ:- ዘወርኃ ጥቅምት ፳፯ ስንክሳር

እግዚአብሔር የመረጠው ጾም

ለተወሰነ ሰዓት ከምግበ ሥጋ የመከልከላችን ዓላማ ራሳችንን መግዛት እንድንችል ነው፡፡ ስለዚህ ‘እየጾምኩ ነው’/የሚል ሰው ካለ ከምንም በፊት ትዕግሥተኛ ፣ ልበ ትሑትና የዋህ ፣ እግዚአብሔርን የሚፈራ ልቡና ያለው ፣ የፍትወታትን ጅረት ከኹለንተናው የሚያስወግድ ፣ ዘወትር በልቡናው ዕለተ ምጽአትን የሚያስብ ፣ በእግዚአብሔር የፍርድ ዙፋን ፊት እንደሚቆም የማይረሳ ፣ በፍቅረ ንዋይ ወጥመድ ተይዞ ምጽዋትን የማይጠላ፣ ወንድሙን ከልቡ የሚወድ ይኹን፡፡ እውነተኛ ጾም ማለት ይኽ ነውና፡፡

“ሰው ራሱን ቢያሳዝን ፣ አንገቱንም እንደ ቀለበት ቢያቀጥን ፣ ማቅ ለብሶ በአመድ ላይ ቢተኛም ይህ ጾም እግዚአብሔር ዘንድ የተመረጠ አይደለም” “ታዲያ እግዚአብሔር የመረጠው ጾም እንዴት ያለ ነው?” ትሉኝ እንደ ኾነም ነቢዩ ኢሳይያስ የእግዚአብሔር አፈ ንጉሥ ኾኖ እንዲህ ሲል ይመልስልናል፡

“የበደልን እስራት ፍታ ፡ ለተራበው እንጀራህን አጥግበው ፡ ድኾችን ወደ ቤትህ አስገብተህ አሳድራቸው ” እንዲህ ስታደርግ ፡- “ያን ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ይበራል፡፡ ፈውስህም ፈጥኖ ይወጣል” ትን.ኢሳ.58 ፥ 5-8

†ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ†

ምንጭ -ኦሪት ዘፍጥረት መፅሐፍ – በገብረ እግዚአብሔር ኪደ