ቅዱሳት ሥዕላት

ክፍል አንድ
ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ
ጥቅምት ፮፤፳፻፲፯ ዓመተ ምሕረት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? በአዲሱ ዓመት የመጀመሪያ ትምህርታችን የሆነውን በፈቃደ እግዚአብሔር ጀምረናል፤ ባሳለፍነው ዓመት በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ስንማር ቆይተን ከዚያም ክለሳ አድርገን ጥያቄና መልስ ማዘጋጀታችን ይታወሳል፡፡ እናንተም ለቀረበላችሁ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ተሳትፋችኋል፤ ጥሩ ውጤት ላስመዘገቡ የማበረታቻ ስጦታንም አበርክተንላቸዋል፡፡ (ሰጥተናቸዋል)፤ እንግዲህ በዚህም ዓመት የምናቀርብላችሁን ትምህርት በደንብ ደግሞ መከታተል እንዳለባችሁ ማሳሰብ እንወዳለን፡፡

መርሳት የሌለባችሁ ሌላው ነገር በዘመናዊ ትምህርታችሁ ከአሁኑ ያልገባችሁን በመጠየቅ፣ የቤት ሥራን በመሥራት፣ በማጥናት ጎበዞችና አስተዋይ ልጆች መሆን እንዳለባችሁ ነው!

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ወላጆቻችን ከእኛ በጣም ብዙ ነገር ይጠብቃሉ፤ ጥሩ ውጤት እንድናመጣ፣ ወደፊት ትልቅ ደረጃ እንድንደርስም ይመኛሉ፤ ስለዚህም እኛ ስንፍናን አርቀን፣ ጨዋታን ቀንሰን፣ በርትተን በመማርና በማጥናት ጎበዝ ልጆች መሆን ይገባናል! ወላጆቻችንን እኛን ለማስተማር ብዙ ነገርን ያደርጋሉ፤ ታዲያ እኛ ጎበዞች በመሆን ደስተኞች ልናደርጋቸው ይገባል፡፡ መልካም! በአዲሱ ዓመት በመጀመሪያው ትምህርታችን ስለ ቅዱሳት ሥዕላት እንማራለን፡፡

ወላጆች ከእኛ ጋር ትምህርት ቤት አይሄዱም፤ ከእኛ ክፍል ገብተው አብረውን አይማሩም፤ ግን ልጆቻችን ትምህርት ቤት ሄደው ተምረው ይመጣሉ ብለው አምነው ይልኩናል! አያችሁ እኛ ትምህርት ቤት ገብተን ተምረን በአግባቡ ወደ ቤት በመመለስ መታመናችንን መግለጥ (ማሳየት) ይገባናል፡፡

ቅዱሳት ሥዕላት

‹‹ሥዕል›› ማለት “መልክ፣ የመልክ ጥላ፣ ንድፍ፣ አምሳል፣ ንድፍ በውኃ፣ በመጽሔት፣ በጥልፍ፣ በስፌት ወይም በቀለም በወረቀት ገዝፎ ተጽፎ፣ ከዕብን፣ ከዕፅ፣ ከማዕድን ታንጦ፣ ተቀርጦ፣ ተሸልሞ፣ አጊጦ የሚታይ የሚዳሰስ ነገር” ነው፡፡›› (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ መዝገበ ቃላት)
ቅዱሳት የሚለው ቃል ደግሞ «ቀደሰ» ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጒሙም “ለየ፣ አከበረ፣ መረጠ” ማለት ነው። ውድ

የእግዚአብሔር ልጆች ቅዱሳት ሥዕላት ለእግዚአብሔር የተለዩ፣ የተቀደሱ፣ ልዩ፣ ምርጥ፣ ንጹሕ እና ጽሩይ የሆኑ የቤተ መቅደሱ መገልገያ ንዋያተ ቅድሳት በመሆናቸው «ቅዱሳት» ተብለው ይጠራሉ። እንዲሁም ደግሞ ቅዱሳት ሥዕላት የቅዱሳንን ታሪክ እና ማንነት በጊዜው ላልነበርን በመንፈስ ዓይን እንድናይ ስለሚያደርጉን፣ አንድም ሥጋዊውን ዓለም ከሚያንጸባርቁ ዓለማውያን ሥዕላት ፈጽመው የተለዩ በመሆናቸው፣ አንድም የቅዱሳን ቅድስና ሥዕላቱን ቅዱስ ስላሰኛቸው፣ አንድም በሥዕላቱ አድሮ እግዚአብሔር ስለሚፈጽመው ገቢረ ተአምራት የተነሣ ሥዕላቱ «ቅዱሳት ሥዕላት» ተብለው ይጠራሉ።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት ሥዕላት ተብለው የሚጠሩት ሐዋርያዊ ትውፊትንና ቀኖናን ጠብቀው የሚሣሉ የቅዱስ እግዚአብሔር፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ የቅዱሳን መላእክት፣ የቅዱሳን ነቢያት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት እና የሌሎች ቅዱሳን ጻድቃን ማንነት፣ ሕይወትና ታሪክ የሚያሳዩ እና የሚወክሉ ሥዕሎች ናቸው፡፡

የቅዱሳንን ሥዕል መሳል ለምን አስፈለገ?

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ቅዱሳን ሥዕላትን በመሳል ለአገልግሎት እንጠቀም ዘንድ ያዘዘን እራሱ የሰማይና ምድር ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ የቃል ኪዳኑን ማደሪያ ታቦት እንዴት እንደሚሠራ ሲነግረው እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ብሎ እንዳዘዘው እናነባለን፤ “ከሥርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን፥ ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርገህ በአንድ ላይ ትሠራዋለህ።” (ዘፀ.፳፭፥፲፱) ይህንንም ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሙሴ መፈጸሙን ሲገልጥልን “ከስርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን፥ ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርጎ በአንድ ላይ ሠራቸው። ክንፎቻቸውን ወደላይ የዘረጉ ሆኑ” በማለት መስክሮታል። (ዘፀ. ፴፯፥፰-፱)

የቅዱሳንን ሥዕል መሳል ያስፈለገው የቅዱሳን መታሰቢያ /ማዘከርያ ስለሆነ፦ እግዚአብሔር አምላካችን ቅዱሳንን ስለ ቅድስናቸው እንዲሁም ስለ እርሱ ብለው ለፈፀሙት ተጋድሎ እንድናስባቸውና እንድንዘክራቸው ትእዛዝ እንዲህ ሲል አስተላልፎልና፤ “በቤቴና በቅጥሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያ ስም እሰጣቸዋለሁ፣ የማይጠፋ የዘለዓለም ስም እሰጣቸዋለሁ፡፡” (ኢሳ.፶፮፥፭)።

በሌላም በኩል (በመጽሐፈ ምሳሌ ፲፥፯) “የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው።” (መዝሙረ ዳዊት ፻፲፪፥፮) “የጻድቅ መታሰቢያ ለዘለዓለም ይኖራል” ተብሎ እንደተመሠከረላቸው በረከታቸውን ለማግኘት ለመታሰቢያቸው መለያቸውን ቅዱሳት ሥዕላት እንጠቀማለን።

ሌላው ደግሞ ከእነርሱ በረከት አልፈን ቅዱሳት ሥዕላት በተሳሉበት በቅድስና ስፍራው እግዚአብሔር ራሱንም ስለምናገኝበት ነው፤ ለሊቀ ነቢያት ሙሴ “በዚያም ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል በሥርየት መክደኛው ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ” ብሎታልና። (ዘፀ.፳፭፥፳፪)

ጠቢቡ ሰሎሞን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ባነፀ (በሠራ) ጊዜ ቅዱሳት ሥዕላትን ሠርቶ ነበር፤ “በቅድስተ ቅዱሳኑም ውስጥ ቁመታቸው ዐሥር ክንድ የሆነ ከወይራ እንጨት ሁለት ኪሩቤል ሠራ፤ ኪሩቤልንም በወርቅ ለበጣቸው፤ በቤቱም ግንብ ሁሉ ዙሪያ በውስጥና በውጭ የኪሩቤልና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸ፤ ሁለቱንም ደጆች ከወይራ እንጨት ሠራ፤ የኪሩቤልንና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸባቸው፥ በወርቅም ለበጣቸው፤ ኪሩቤልንና የዘንባባውን ዛፍ በወርቅ ለበጣቸው፤ የኪሩቤልንና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸባቸው፤ በተቀረጸውም ሥራ ላይ በወርቅ ለበጣቸው” ተብሎ ተጽፏል። (፩ኛ ነገ ፮ ፥፳፫-፴፭)።

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! በዘመነ ሐዋርያት ደግሞ ቅዱስ ሉቃስና ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ቅዱሳት ሥዕላትን ይሥሉ ነበር። ነባቢ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ የተመለከታትን የቃል ኪዳኑ ታቦት ነው፡፡ (ራእይ ፲፩፥፲፱)

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለዛሬ ስለ ቅዱሳት ሥዕላት የቃሉን ፍቺ እና ቅዱሳት ሥዕላት ለምን እንደሚሳሉ በመጠኑ ተመልክተናል፤ በቀጣይ ስለ ቅዱሳት ሥዕላት ጥቅምና አሳሳል እንመለከታለን፡፡ (ምንጭ ኦርዶክሳዊ ቅዱሳት ሥዕላት አሳሳል)
ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ በትምህርታችሁ በርትታችሁ ተማሩ! ለወላጅ መታዘዝን፣ ለሰዎች መልካም ማድረግን እንዳትረሱ፤ በሰንበት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መንፈሳዊ ትምህርትንም ተማሩ፡፡ ቸር ይግጠመን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

የንሂሳው ኮከብ

ጥቅምት ፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

በዐፄ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት፣ ዐሥራ ሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመጡት ግብጻዊው ቅዱስ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የትውልድ ስፍራቸው በላዕላይ ግብጽ ንሂሳ እንደሆነ ገድላቸው ይጠቅሳል፡፡

አባታቸው ስምዖን እናታቸው አቅሌስያ የተባሉት ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ሰዎች እንደነበሩ ሆኖም ልጅ አጥተው ፴ (ሠላሳ) ዘመን ሲያዝኑ መኖራቸውንም ታሪካቸው ያነሣል፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀንም እናታቸው አቅሌሲያ ቤተ እግዚአብሔር ገብታ ከሥዕለ ሥላሴ ሥር ወድቃ ስትማጸን ክብሩ ከሰማይ ከፍታ የሚበጥ ልጅ እንኪ ተቀበይ የሚል ድምጽ ሰማች፡፡ ‹‹ሥልጣኑ ከሰማይ ከፍታ ከፍ የሚል ንጽሕናው ከሚካኤል ከገብርኤል የሚተካከል ክህነቱ እንደ መልከጼዴቅ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ እንደ ነቢይ ኤልያስ የሆነ ልጅ እንቺ ተቀበይ›› አላት፡፡ አቅሌስያም በመጋቢት ፳፱ ቀን ፀንሳ በታኅሣሥ ፳፱ ቀን ደም ግባቱ እጅግ የሚያምር ወንድ ልጅ እንደወለደች መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሰው አምሳል መጥቶ ‹‹የዚህ ልጅሽ ስሙ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ይሁን›› አላት፡፡ ወዲያውም ሕፃኑ ተነሥቶ ከእናቱ ጭን ወርዶ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ሦስት ጊዜ ሰገደ፡፡ ዳግመኛም ‹‹ከጨለማ ወደ ብርሃን ለአወጣኸኝ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን›› አለ፡፡

አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተፀነሱት መጋቢት ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን፣ የተወለዱት ደግሞ ታኀሣሥ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ)  ነው፡፡ አባታችን ዓይን በገለጡ ጊዜ ከሚታይ ነገር ላይ እንዲያርፍ እርሳቸውም በተወለዱ ጊዜ ተነሥተው «ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ዘዓውፃእከኒ እምጽልመት ውስተ ብረሃን» ብለው አመስግነዋል። አባታችን ለአምላክ ሰግደው አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ካመሰገኑ በኋላ እናታቸው አላቀፈቻችውም፤ ጡትም አልጠቡም፡

ጻድቁ አባታችን አኗኗራቸው እንደ መላእክት በምድረ በዳ የነበር፣ በዝቋላ ተራራ ባለው ባሕር ውስጥ ፻ (መቶ) ዓመት ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ሰዎች ምሕረትን የለመኑና ምሕረትን ያሰጡ ቅዱስ ናቸው፡፡ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከ፭፻ (አምስት መቶ ዓመታት) በላይ በዚህ ምድር ላይ መኖራቸውንና ከትግራይ እስከ ሸዋ ባለው ክፍል ተዘዋውረው ማስተማራቸውን ገድላቸው ያትታል፡፡ በዚህም ምክንያት ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስንና ምድረ ከብድ ገዳማትን መትከላቸውን ታሪካቸው ያሳያል፡፡ ያረፉት በዐፄ ሕዝብ ናኝ ዘመን መጋቢት አምስት ቀን ነው፡፡ የምሕረት ቃልኪዳን የተቀበሉት ደግሞ ጥቅምት አምስት ቀን ነው፡፡ የከበረው በድነ ሥጋቸውም በምድረ ከብድ ይገኛል፡፡ ጻድቁ በትግራይ አቡዬ፣ በአማራው አቡነ፣ በኦሮሞዎች ዘንድ ደግሞ አቦ በመባል ይታወቃሉ፡፡

የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፤ በጸሎታቸው ይማረን!

ምንጭ፡ – ገድለ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ተስፋ ገብረ ሥላሴ ፲፱፻፺፪ .

 

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

ያለምንም ደመወዝ በራሳቸው ዓቅም በግብርና እየተዳደሩ ቤተ ክርስቲያንን በጥሩ ሰብእና በንጽሕና እና በቅድስና ጠብቀው ያስረከቡ እልፍ አእላፍ አበው እንዳልነበሯት ዛሬ የተሻለ ኑሮና ደመወዝ እያገኘን እግዚአብሔርን እንደቀኖናው በጥንቃቄ ማገልገል አቅቶናል” ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ

ጥቅምት ፬/፳፻፲፰ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ

የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ

የአዲስ አበባና ሐድያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የየመምሪያውና የየድርጅቱ ኃላፊዎች ፣

ከሀገር ውስጥና ከውጭ ሀገር የመጣችሁ የየሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጆችና የየክፍሉ ተወካዮች፣

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ኃላፊዎች፣

የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችና ተወካዮች

የምእመናንና የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች፣

በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ ጉባኤ የተገኛችሁ ክቡራና ክቡራት

እግዚአብሔር አምላካችን ዓመቱን ጠብቆ በከፍተኛ ጉጉት ለምንጠብቀው አርባ አራተኛው የሰበካ ጉባኤ አጠቃላይ መንፈሳዊ ዓለም ዓቀፍ ጉባኤ ስላደረሰን ክብርና ምስጋና ለእርሱ እናቀርባለን፡፡ እናንተንም እንኳን በደኅና መጣችሁ እንላለን፡፡

“ዑቁ እንከ ዘከመ ተሓውሩ ከመ ጠቢባን በንጽሕ ወአኮ ከመ ዓብዳን፤ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንደ ጥበበኞች እንዴት በንጽሕና እንደምትመላለሱ ዕወቁ” (ኤፌ.፭፥፲፭)፤ ሁሉንም መስጠትና መንሣት የሚችለው እግዚአብሔር አምላክ ጥበብን ለሰው ልጆች ሰጥቶአል፤ የሚሰጠው የጥበቡ ደረጃ የተለያየ ቢሆንም እግዚአብሔር ከጥበብ ባዶ አድርጎ የፈጠረው ግን የለም፤ የእግዚአብሔር ስጦታዎች ለፍጡራን ሲሰጡ ሊጠቀሙባቸው እንጂ እንዲሁ በከንቱ ሊያባክኑዋቸው አይደለም፡፡

ቅዱስ መጽሐፍ ስለ ጥበብ አስፈላጊነት በብዙ ቦታ ያስተምራል፤ በተለይም ጠቢቡ ሰሎሞን “ጥበብ ትኄይስ እምኲሉ መዛግብት ወኲሉ ክብር ኢመጠና ላቲ፤ ከሀብት ሁሉ ጥበብ ትበልጣለች፤ ክብርም ሁሉ አይመጣጠናትም” በማለት የጥበብ ብልጫ ተወዳዳሪ የሌላት እንደሆነች ያስገነዝበናል፤ እግዚአብሔርም ሥራውን ሁሉ በጥበብ እንደሚሠራ “ወኲሎ በጥበብ ገበርከ፤ ሁሉንም በጥበብ አደረግህ” በሚል ተጽፎ ይገኛል፤ እግዚአብሔር ሥራውን በጥበብ እንደሚሠራ፣ እኛንም በጥበብ መሥራት እንዳለብን ሲያስተምረን፣ ‹‹ኩኑ ጠቢባነ ከመ አርዌ ምድር እንደ እባብ ብልሆች ሁኑ›› ብሎናል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት!

ክቡራን የጉባኤው ተሳታፊዎች!

ዘመንና ቦታ ሳይገድበን ምንጊዜም ሥራችንን በጥበብ መሥራት እንዳለብን ቢታወቅም ዛሬ ላይ ከምን ጊዜውም በበለጠ በጥበብ መመላለስ የሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ እንገኛለን፤ የዛሬዎቹ ችግሮች በአንድ አካባቢ ብቻ ያሉ ሳይሆኑ ዓለም ዓለፍ ቅርጽ ያላቸው እንደሆኑ ታላላቅ መሪዎች ሳይቀሩ በዓለም መድረክ ላይ ስሞታ ሲያቀርቡ በዓይናችን አይተናል፤ በጆሮአችንም ሰምተናል፤ በሁኔታውም የክርስትና ሃይማኖት በአጠቃላይ በተለይም ደግሞ የኦርቶዶክሱ ወገን የችግሩ ገፈት ቀማሽ እንደሆነ እየተስተዋለ ነው፡፡

እኛም የዚሁ ወገን አካል በመሆናችን የችግሩ ቀማሽ መሆናችን አልቀረም፤ በየቀኑ ካህናትና ምእመናን ይገደሉብናል፤ አብያ ክርስቲያናት ይቃጠሉብናል፤ የእምነትና የኅሊና ነጻነት በእጅጉ የሳሳ ሆኖብናል፤ አላስፈላጊ ጫናዎችም በዝተውብናል፤ ከውጭና ከውስጥ በተቀነባበረ ስሌት የቤተክርስቲያናችንን ስም ማጥፋት የዕለት ተግባራቸው ያደረጉ አካላት ተበራክተዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ከነባሩና ረጅም ዘመን ካስቈጠረው ሰፊ ማእዷ እያበላቻቸው ያለች መሆኗን ዘንግተው እንብላሽ፣ እንዋጥሽ የሚሉዋት ወገኖች በዝተዋል፣ በእነዚህና በሌሎች ምክንያቶች አባቶች እንደልብ ተንቀሳቅሰው መሥራት የማይችሉባቸው አጋጣሚዎች እየተፈጠሩ ነው፤ የወለጋው ችግር ለዚህ በዋናነት ተጠቃሽ ነው፡፡

ታድያ እነዚህን ፈተናዎች ለማለፍ ጥበብ ያስፈልጋል፤ ነገር ግን ጥበብ መከተል ማለት ዝም ብሎ ማለፍ ወይም አይተው እንዳላዩ ሆኖ መኖር ማለት አይደለም፤ በጥበብ መመላለስ ማለት ከሁሉ በፊት ችግሮችንና የችግሮችን መንሥኤዎች በአግባቡ መረዳትና መለየት መቻል ነው፤ ከዚያም ራስን ለከፋ አደጋ በማያጋልጥ መልኩ የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም መሸጋገር መቻል ነው፤ በዚህ ዘመን እንዲህ ያለ ጥበብ መጠቀም የግድ ያስፈልጋል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት!

ክቡራን የጉባኤው ተሳታፊዎች! ቤተ ክርስቲያናችን እየተፈተነች ያለችው ከውጭ ብቻ ሳይሆን ከውስጥም ጭምር እንደሆነ መካድ የለብንም፤ ንጽሕትና ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥር የሰደደ የቅድስና ሕይወትና በፈሪሀ እግዚአብሔር የተቃኘ ሥነ ምግባር ያላት ቤተ ክርስቲያን ናት፤

በአሁኑ ጊዜ ግን እነዚህ ሁሉ ቦታቸውን እየለቀቁ ያሉ መስለዋል፤ ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ ታሪኳ ሲያስተምሩም ሆነ ሲማሩ፣ ሲመንኑም ሆነ ሲመነኲሱ፣ ሲቀድሱም ሆነ ሲያስቀድሱ ያለምንም ደመወዝ በራሳቸው ዓቅም በግብርና እየተዳደሩ ቤተ ክርስቲያንን በጥሩ ሰብእና በንጽሕና እና በቅድስና ጠብቀው ያስረከቡ እልፍ አእላፍ አበው እንዳልነበሯት ዛሬ የተሻለ ኑሮና ደመወዝ እያገኘን እግዚአብሔርን እንደቀኖናው በጥንቃቄ ማገልገል አቅቶናል፤ ምእመናንም በዚህ ምክንያት እየተሰናከሉ እንደሆነ እየተስተዋለ ነው፡፡ ሚድያውም ስሕተቶችን ወደ ውጭ በማውጣት ሰድቦ ለሰዳቢ እየዳረገን ነው፤ ይህ ሊሆን የቻለው የቤተ ክርስቲያን ሀብትና ንብረት በአግባቡ በመያዝ ለታለመለት ዓላማ ማዋል አለመቻላችን ነው፤ ይህ ችግር ባለበት ከቀጠለ ሌላ ጦስ ይዞብን እንዳይመጣ ሁነኛ ለከት ማኖር የግድ ይሆናል፡፡

የሰበካ ጉባኤ አደረጃጀት የቤተ ክርስቲያናችንን ሀብተ ጸጋ በማሳደግ ረገድ አስተማማኝ ስልት እንደሆነ በተግባር የተረጋገጠ ነው፤ ሆኖም ሲጀመር ሳለ የነበረ መነቃቃት በአሁኑ ጊዜ የቀነሰ መስሎ ይታያል፤ አሁን በቤተ ክርስቲያን ሰፊ ሽፋን ይዞ የሚገኘው የሙዳየ ምጽዋት ገቢ እንጂ የሰበካ ጉባኤ አስተዋፅኦ እንደአይደለ ሁላችንም እናውቃለን፤ በተለይም በከተሞች ውስጥ ነገሩ ጎልቶ ይታያል፡፡

ይህ የሆነበት ምክንያት ምናልባትም በየደረጃው በኃላፊነት ያለን ሰዎች ሻል ያለ ደመወዝ ስለምናገኝ የሰበካ ጉባኤው ተልእኮ ከሚፈለገው ደረጃ ላይ  የደረሰ መስሎን ይሆናል፤ ነገር ግን ከሰማንያ ከመቶ ያላነሰ የገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ መምህርና ካህን አሁንም ያለ ደመወዝ የሚኖር ነው፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከቤተ ክርስቲያኑ ሊያገኘው የሚገባ የበጎ አድራጎት የጤና የትምህርትና የማኅበራዊ ዋስትና አገልግሎት በሚጠበቀው ደረጃ ሊያገኝ አልቻለም፤ የገዳማትና የአብነት ት/ቤቶች ችግሮችም በነበሩበት የልመና ኑሮ እየቀጠሉ ነው፤ በውጤቱም በችግር የሚኖሩ ገዳማት የተዘጉ የአብነት ት/ቤቶችና አብያተ ክርስቲያናት ከተበራከቱ ሰነባብቶአል፡፡

ታድያ ይህንን ሁሉ መልክ ማስያዝና ቤተ ክርስቲያንን ለቀጣዩ ትውልድ ማሸጋገር የሚቻለው በጥበብና በጥበብ ብቻ መሥራት ሲቻል ነው፤ ይህንን ችግር መፍታት የሚያስችል ጥበብ ደግሞ በዘመናችን አለ፤ የጠፋው ቅንነቱና ፈቃደኝነቱ ነው፡፡

በየዓመቱ የምናካሄደው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ እንደነዚህ ያሉትን ችግሮች መቅረፍ የሚያስችል ካልሆነ ተሰብስበናል ማለቱ ብቻ ትርጉም ሊኖረው አይችልም፤ ስለሆነም ከዚህ በላይ የተጠቃቀሱና ሌሎችም የቤተ ክርስቲያናችን ተግዳሮቶች ካሉ በዚህ ጉባኤ በማንሣት በማየትና በመገምገም ለቤተ ክርስቲያን አሻጋሪና ጥበባዊ ውሳኔ እንዲያሳልፍ አባታዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም

ዓመታዊው ዓለም ዓቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በጸሎተ ወንጌል የተከፈተ መሆኑን በእግዚአብሔር ስም እናበሥራለን፡፡

መልካም ጉባኤ ያድርግልን!

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ !!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር !!!

አሜን!!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

የእምነት አርበኛ

መስከረም ፳፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ጽኑ ሰማዕት የእምነት አርበኛ፣ ጠላትን ተዋጊና ድል አድራጊ እናታችን ቅድስት አርሴማ የሰማዕትነት አክሊል የተቀበለችበት የከበረች በዓል መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በድምቀት ይከበራል፡፡

እጅግ መልከ መልካም የነበረችው ሮማዊቷ ዕንቁ ከልጅነቷ ጅምሮ ራሷን በድንግልና ሕይወት ጠብቃ የኖረች ቅድስት እንደነበረች ታሪክ ይነግረናል። በዘመኑ ነግሦ የነበረው ከሀዲው ድዮቅልጥያኖስም መልኳ ውብ የሆነች ድንግል ሊያገባ ፈልጎ ከየሀገራቱ ቆንጆ መርጠው ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮቹን አዘዛቸው፡፡ እነርሱም በፍለጋቸው በሮሜ አገር ባለች ቤተ ክርስቲያን ቅድስት አርሴማን በማግኘት ሥዕሏን ሥለው ለንጉሡ ላኩለት፡፡ እርሱም በእጅጉ ተደስቶ እንዲያመጧት በማዘዝ ወደ ሰርጉም እንዲመጡ ለመኳንንቱ ላከ፡፡ እርሷና አብረዋት የነበሩትም ደናግል ይህነን በሰሙ ጊዜ በማዘን ድንግልናቸውን ይጠብቅላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር በመለመን ከሮም ተነሥተው በስውር የንጉሥ ድርጣድስ ግዛት ወደነበረችው ወደ አርመን ሸሽተው ሄዱ፡፡

ቅድስት አርሴማም ወደ አርመንያ ሀገር በገባች ጊዜ ከሃድያኑ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የሚያምኑትን ክርስቲያኖችን ላይ መከራን ሲያጸኑባቸው ተመለከተችና አምላካችን ክርስቶስ “እኔ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የማምን ክርስቲያን ነኝ” በማለት መሰከረች፡፡ የመልኳን ደም ግባትም በማየት ንጉሥ ድርጣድስም ለራሱ ስለተመኛት አምላክን እንድትክድ በብዙ ሽንገላን ሊሸነግሏት ቢሞክሩም አልሆነላቸውም፤ ፈርታ ትክዳለችም ብለው በማሰብ ክርስቲያኖች ለአናብስት ወደሚጣሉበት አደባባይ በመውሰድ የተራቡ አናብስትን በላያቸው ለቀቁባቸው፤ ቅድስት አርሴማ በዚህ ጊዜ ወደ አምላክ ጸሎት አደረገች፤ ድንቅ በሆነው ተአምሩም እግዚአብሔር አናብስቱ ወደ ቅድስቷ ሳይሆን  ወደ ንጉሡ ወታደሮች በመወርወር ብዙዎችን እንዲገድሉ አደረገ፤ በኋላም ተንበርክከው ሰገዱላት፡፡

ንጉሡም በሌላ መንገድ የቅድስት አርሴማን ሐሳብ ለማስቀየርና በግድ ለጣዖታቱ እንድትሰግድ ለማድረግ አሳስሮ አማልክቱ ወዳሉበት ቤተ ጣዖት ወሰዳት፤ ይህን ጊዜ በመስቀል ምልክት ብታማትብ በጣዖታቱ ላይ አድረው ሰዎችን የሚያስቱ አጋንንት እየጮኹ ሲወጡ ጣዖታቱ በመላ እየተሰባበሩ ወድቁ፤ ዳግመኛም እስር ቤት አስገብቶ ሊያስርባት ቢጥርም የእግዚአብሔር መልአክ እንደ ነቢዩ ኤልያስ ኅብስትን መገባት፡፡ ቀጥሎም ንጉሡ ወዳለበት እየጐተቱ ወስደው ሲያቆሟት ንጉሡ ይዞ ወደ እልፍኙ ሊያስገባት ከአደባባይ ተነሥቶ ድንግል አርሴማን በያዛት ጊዜ ቅድስቷ በላይዋ ላይ ባደረው የእግዚአብሔር ኀይል በምድር ላይ ጣለችው፤ ያን ጊዜ በንዴትና በአፍረት አገልጋዮቹን ራሳን እንዲቈርጡ አዘዛቸው። በዚህ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምን አስከትሎ ተገለጸላት። ስሟን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ምሕረትን እንደሚያደርግ ቃል ኪዳንን ገባላት፡፡ በክርስቶስ ፍጹም ፍቅር፣ በእምነት ጽናትና ተጋድሎ ዕጹብ ድንቅ የሆነው ገድሏን ፈጽማ አንገቷን በመሰየፍ መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጅታለች።

የቅድስት አርሴማ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፤ በጸሎቷ ይማረን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

የአበባ ወር

መስከረም ፳፮፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ጊዜ የተለያዩ ተፈጥራዊ ኩነቶችን ያስተናግዳል፤ በዓለም ላይ በሚከሰቱ የወቅቶች መፈራረቅም ምድር አንዳንዴ ስትበለጽግ ሌላ ጊዜ ደግሞ ትራቆታለች፡፡ በክረምት ወራት በሚዘንበው ዝናብ ስትረጥብ በበጋ ደግሞ በፀሐይና በሙቀቱ ትደርቃለች፡፡ በዘመነ መጸው በነፋሳት ስትናወጥ ፈክተው የሚያብቡት አበቦች ግን ያስውቧታል፡፡

ቅዱሱ ሰው አባ ጽጌ ድንግል የአበቦችን ዕጹብ ድንቅ ተፈጥሮና የላቀ ዋጋ በማወቁ ሳይሆን አይቀርም ከአበቦች ሁሉ በሚበልጥ አበባ ለምንመስላት ድንግል ማርያም አበቦችን ያበረከተላት፡፡ በዐሥራ አራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሱት ሊቁ የደረሱት የማኅሌተ ጽጌ ድርሰት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ቀን ድረስ ባለው ወቅት የእመቤታችን ከልጇ ጋር ወደ ግብፅ ብሎም ወደ ኢትዮጵያ መሰደድ እና መንከራተት እንዘክርበታለን፡፡

የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤አሜን!

የኒቂያ ጉባኤ

መስከረም ፳፪፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የአርዮስ ክህደት በተስፋፋበት በ፫፻፳፭ ዓ.ም የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት የማይቀበሉ መናፍቃን ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ ጊዜውም ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ስለነበር ንጉሡ በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሄድ በየአገሩ ለነበሩ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ሊቃውንቱ በሱባኤና በጸሎት ከቆዩ እስከ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይሁን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡

የቅዱሳን አባቶቻችን ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

 

ግሸን ማርያም

መስከረም ፳፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የግሸን ማርያም ደብር መመሥረት ከግማደ መስቀል ጋር የተያያዘ ዋነኛ ምክንያት አለው፡፡ ግማደ መስቀሉ ከእስክንድርያ የገባው መስከረም ፲ ቀን ቢሆንም ኢትዮጵያ ‹‹ግሸን አምባ›› የገባበት፣ መቅደስ ተሠርቶ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረውና ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ለመላው ኢትዮጵያ በጽሑፍ በመዘርዘር የገለጹበትም መስከረም ፳፩ ቀን ነው፡፡

በየዓመቱ መስከረም በባተ በ፳፩ኛው ቀንም በግሸን ደብር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች ከበረከተ መስቀሉና ከቅዱሳን ዐፅም በረከት ለማገኘት ከየክፍለ ሀገራቱ እየመጡ ያከብራሉ፡፡ ምእመናንም በግሸን ማርያም ለመገኘት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ይሄዳሉ፡፡ ኃጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ሁሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ‹‹ጤፉት›› በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡

አምላካችን እግዚአብሔር ከበረከተ መስቀሉ ያሳትፈን፤ አሜን!!!

 

መስቀል

መስከረም ፲፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ፍጹም ድንቅ የሆነው የጌታ ፍቅር የተገለጸበት፣ ሰላም የተበሠረበት፣ የነጻነታችን መገለጫ፣ የድኅነታችን መረጋገጫ ቅዱሱ መስቀል የተገኘበት ዕለት የከበረ ነውና በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ የመጀመሪያው ሰው አዳም በበደሉ ምክንያት ዕዳውን ይከፍለለት ዘንድ ሰው ሆኖ በሞቱ ሕይወትን የሰጠን አምላክ በመስቀል ተሰቅሎ ስለሆነም የመስቀሉ ነገር ለክርስቲያኖች ብዙ ትርጒም አለው፡፡

ለሰው ዘር በሙሉ በተገባለት ቃል ኪዳን መሠረት ጌታችን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ፣ ሰው ሆኖ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ድኅነትን ለሰው ልጆች ሰጥቶ፣ በመስቀሉ ተጣልተው የነበሩ ሰባቱን መስተፃርራን (ሰውና እግዚአብሔርን መላእክትና ሰውን፣ ነፍስና ሥጋን፣ ሕዝብና አሕዛብን) አስታርቋል፡፡

በሐዲስ ኪዳን መስቀል የመዳን ምልክት መሆኑ የተረጋገጠበት በክርስቶስ ደም የተቀደሰ፣ የጠብ ግድግዳን ያፈረሰ፣ ቅድስናና ክብር ያለው የአበው ተስፋ የተፈጸመበት፣ ሰው ከውድቀቱ የተነሣበት መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ ነቢዩ ዳዊት ‹‹እግዚአብሔር ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማእከለ ምድር … እግዚአብሔር ግን ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድርም መካከል መድኃኒትን አደረገ›› (መዝ. ፸፫፥፲፪) እንዳለው መድኃኒት የሆነው አምላካችን በመስቀሉ አዳነን፡፡ (ዮሐ. ፲፱፥፲፯፣ኤፌ. ፪፥፲፮፣ ቆላ. ፩፥፳)

ከበዓሉ በረከት ይክፈለን፤ አሜን!!!

 

የአበባ በዓል

 

መስከረም ፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ምድር በአበባ በምታሸበርቅበት በክረምት መውጫ በተለየ መልኩ የሚከበረው ተቀጸል ጽጌ (የአበባ በዓል) መስከረም ፲ ቀን ነው፡፡ ተቀጸል ጽጌ ማለትም (አበባን ተቀዳጀ) የሚባለውን በዓል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታከብራለች፡፡

በአበባ በምትዋብበት ወቅት ምድር በአረንጓዴ ተክሎች በምትዋውበት፣ በዕፅዋቶች ልምላሜ በምትደምቅበት፣ በአዝእርቶች ቅጠል ልምላሜ በምትሸለመብበት ጊዜ በዘመኑ የነበሩት የኢትዮጵያ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል በመስከረም ፲ በአረንጓዴ፣ በቢጫ እና በቀይ ቀለም ደምቆ የጽጌረዳ አበባ በመሰለ ፈርጥ የተሠራ ዘውድ ደፍተው በአደባባይ በሠራዊቶቻቸው ታጅበው የክረምቱን ማለፍ እያበሰሩ በክብር በሰዎች መካከል ይገኛሉ፡፡

በዚያን ጊዜም በወቅቱ የነበሩት ካህናት በዝማሬ ምእመናኑ በእልልታ የክረምቱን ማለፍ የዘመነ ጸደይን መተካት እያገለጹ እግዚአብሔር አምላክን ያመሰግናሉ፡፡ ዐፄ ገብረ መስቀል በዚሁ  ግብር ያበላሉ፡፡ ተቀጸል ጽጌ በዚህ መልኩ እየተከበረ አስከ ዐፄ ዳዊት ፲፫፻፺፭ ዓ.ም እንደደረሰ ታረክ ያወሳናል፡፡ ከዚህም በኋላ በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ከሊፋ የሚባል የግብጽ ንጉሥ ተነሥቶ በግብጻውያን ክርስቲያኖች ላይ ጭቆና ሲያደርስባቸው ፓትርያርካቸውን ጭመር በማሰር በብዙ አሠቃያቸው፡፡

ንጉሡም ወደ ግብጽ ንጉሥ “እርዳን፤ እምነትህ እምነታችን ነው” የሚል መልእክት ላኩ፡፡ ከዚያም ሠራዊቱን አስከትሎ የኢትዮጵያን ድንበር አልፎ ሱዳን እና የግብጽ ድንበር ላይ ስናር በሚባለው ቦታ ሆኖ ለግብጹ መሪ “በክርስቲያኖች ላይ የሚያደርሰውን መከራ የማታቆም ከሆነ ዘምቼ እዋጋሃለው፤ አባይንም እገድባለሁ” በማለት መልእክት ይልክበታል፡፡ ከዚያም የግብጹ መሪ በክርስቲኖች ላይ የሚያደርሰውን ግፍና መከራ አቆመ፡፡

የግብጽ ክርስቲኖችም ነጻነታቸውን በማግኘታቸው ደስ ተሰኝተው ለኢትዮጵያው ንጉሥ እጅ መንሻ አድርገው ወርቅ፣ ብር እና አልማዝ ይልካሉ፤ ንጉሡ ዐጼ ዳዊት ግን “ይህ ምን ያደርግልኛል፤ ወርቅማ በሀገሬም ሞልቶኛል፤ የምፈልገው የክርስቶስን ግማደ መስቀል የቀኝ እጁ ያረፈበትን መስቀል ነው” በማለት ይመልሳል፡፡ ምንም እንኳን ለመስቀሉ ያላቸው ፍቅር ታላቅ ቢሆንም በእምነታቸው ተከብረው እንዲኖሩ ያደረጋቸው የንጉሡ የዐፄ ዳዊት እርዳታ ስለሆነና አሁንም ከንጉሡ ጋር ካልተባበሩ የግብጹ መሪ ሊያጠቃቸው ስለሚችል ዐጼ ዳዊትን ለማስደሰት የክርስቶስን ግማደ መስቀል ከልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳት ጋር ላኩላቸው፡፡ ሆኖም ንጉሡ መስቀሉን ወደ ኢትዮጵያ ሳያስገቡ ያርፏሉ፡፡

ለ፵፯ ዓመትም መስቀሉም በዚያው ቆይቶ ንጉሡ ልጅ በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ በ፲፬፻፵፫ ዓ.ም መስከረም ፲ ቀን ወደ ኢትዮጵያ ገባ፡፡ ለመስቀሉ ክብር እንዲሆን በማሰብም በመስከረም ፳፭ ቀን የሚከበረው የተቀጸል ጽጌ በዓል መስከረም ፲ ቀን እንዲከበር ተወሰነ፡፡ በዚህም ሁኔታ እስከ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት መጨረሻ “ተቀጸል ጽጌ፣ የዐፄ መስቀል፣ ሐፀጌ” በማለት እየተከበረ እስከ ፲፱፻፷፮ ቆይቶአል፡፡  በቤተ መንግሥት በመሪዎች ደረጃ ግን መከበሩ አልቀጠለም፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግን ቅዱስ ፓትርያርኩ እና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ባሉበት የተወሰኑ አድባራት ካህናት አባቶች፣ መዘምራን በተገኙበት እስከ አሁን ድረስ ታከብራለች፡፡ በዓሉ መስከረም ፲ ቀን በየዓመቱ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ዛሬም ይከበራል፡፡

ከመስቀሉ በረከት ሁላችንንም ያሳትፈን፤ አሜን!

 

 

 

 

ተአምረኛዋ ሥዕል

መስከረም ፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

እጅጉን የሚያስደንቀው የአምላክ ሥራ የተገለጠበት፣ ለሰው ልጆች ተስፋ፣ ፈውስ ሥጋ እንዲሁም ፈውስ ነፍስን ሊሰጠን በፈቀደ እርሱ ድንቅ ተአምራትን በምድር አደረገ፤ ጌታ በትስብእቱ በዓለም ተገልጦ ካደገጋቸው ተአምራትም በተጨማሪ እርሱ ካረገ በኋላም በሰዎች አድሮ ላይ አድሮም ይሁን በተለያዩ መንገዶች ዕጹብ ሥራውን አሳይቶናል፡፡

ከዚሀ ሁሉም በበለጠ መልኩ በክብርት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም የተደረገው ምሥጢር እጅግ ይልቃል፤ ነገረ ድኅነቱን የፈጸመባት እመቤታችን ለአዳም ዘር በሙሉ ተስፋ በመሆኗ ጌታ ከእርሷ በለበሰው ሥጋ ተገልጦ ያደረገልንን ለመግለጽ ቃላት ባይኖርም ምስጋና ግን ማቅረብ የሁላችንም ፈንታ ነው፡፡ አልፎ ተርፎም እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታ ካረገች በኋላ ድንቅ ተአምርም በእርሷ ተደርጓል፡፡ ቅዱሳት መጽሐፍት በተለያዩ ጊዜ እመቤታችን ያደረገችውን ተአምር ገልጸው ጽፈዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል በመጽሐፈ ስንክሳር መስከረም ፲ ቀን ተመዝግቦ የምናገኘው አንድ ተአምረኛ ሥዕል እንዳለ ነው፤ ታሪኩም እንዲህም ይነበባል፡፡

አንዲት ማርታ የምትባል ሴት እመቤታችን ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ሁሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ ኢትዮጵያዊ መነኰስ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡ ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡

አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጉዞ ጀመሩ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ሲደርሱ ወንበዴዎች ተነሱባቸው፡፡ ሊሸሹ ሲሉም ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ኹሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም ፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡

በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፤ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ሆነህ ነው?›› ስትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር ሁሉ ነገሯት፤ ራሳቸውንም ገለጡላትና ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡ ሥዕሏም ቅዱስ ሉቃስ የሳላት ነበረች፡፡

 

አንኳን ለበዓለ ጼዴንያ ማርያም አደረሳችሁ!