ተስፋ መቁረጥ የኅሊና ሞት!

                                                                                                                                                                  ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ 

ታኅሣሥ ፲፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ኅሊና የሚለውን ቃል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ “የአፍአ፣ የውስጥ ሕዋስ፣ ረቂቅ፣ ውሳጣዊ፣ ተነሣሽ፣ ተንቀሣቃሽ” በማለት ይገልጡታል፤ (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ገጽ ፬፻፸፯)

ኅሊና ጥሩና በጎውን፣ ትክክልና ስሕተቱን የሚለይ የአእምሮ ክፍል ነው፤ የራስ መመዘኛ፣ ክፉና በጎውን መለያ፣ የግላዊ ሂስ ማቀነባበሪያ፣ የነፍስ ክፍል በማለትም ይተነትኑታል፡፡ ኅሊና በጎውንና ክፉውን የምንለይበት መልካም ስንሠራ ሰላም፣ መረጋጋት እንዲሰማን፣ ስንበድልና ሕግ ስንተላለፍ ወቀሳን የሚያደርስብን ነው ፤ ‹‹..እነርሱም ይህንን ሲሰሙ ኅሊናቸው ወቀሳቸውና ከሽማግሌዎች ጀምሮ  እስከ ኋለኛዎቹ አንድ አንድ እያሉ ወጡ ….›› (ዮሐ.፰፥፱) አበው ኅሊናን  ‹‹እግዚአብሔር በሰው ልጅ ውስጥ ያስቀመጠው እውነተኛ ዳኛ ነው›› በማለትም ይገልጡታል፡፡ ዛሬ በዚህ መልእክታችን ማስገንዘብ የፈለግነው ስለ ኅሊና ምንነት በጥልቀት መመልከት ሳይሆን ተስፋ መቁረጥ ስለሚያመጣብን የኅሊና ሞት ነው፡፡

ተስፋ ለክርስቲያኖች ሕያው ነው፤ ግዑዝ አይደለም ወይም ቁስ አይደለም ሕይወት ያለው ነው እንጂ፤ ‹‹…በእግዚአብሔር ክብርም ተስፋ እንመካለን፤ ይህም ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ፣ ትዕግሥትም ፈተናን፣ ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን በመከራችን ደግሞ እንመካለን፤ በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍረንም›› (ሮሜ ፭፥፲፭) ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጠው፤ ተስፋ የእምነታችን ምንጭ ነው፤ የተስፋ ምንጭ ወይም መገኛው ደግሞ የሁሉ ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው፤ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ምእመናን በላከው መልእከቱ ‹‹…የተስፋ አምላክም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በተስፋ እንድትበዙ በማመናችሁ ደስታንና ሰላምን ሁሉ ይሙላባችሁ…›› (ሮሜ ፲፭፥፲፫) በማለት ገልጾልናል፡፡

ሰው ምግብ ሳይመገብ፣ ውኃም ሳይጠጣ ለተወሰነ ጊዜ መቆየት ይችላል፤ አየርም አጥሮት እንዲሁ ለደቂቃዎችም  ቢሆን በሕይወት የመኖር ዕድል አለው፤  ተስፋ ከቆረጠ ግን ለሰከንድ መኖር አይችልም፡፡ በዚህ ምድር ላይ እየተቸገርን፣ በፈተና ወጀብ ታጅበንም፣ እየተሰደድንም እየኖርን ያለነው ነገን ከዛሬ የተሻለ ሆኖ እናገኘዋለን በሚል ተስፋ ነው፤ ተስፋ ባይኖረን  ከትናንት አልፈን ዛሬን ባላየናት፣ ዛሬ ላይ ቆመን ነገን ባልናፈቅናት ነበር፡፡

ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ በላከለት አባታዊ ምክሩ የኅሊናን መሞት ምን ያህል ለጥፋት እንደሚዳርግ እንዲህ ይገልጠዋል፤ ‹‹…እምነትና በጎ ኅሊና ይኑርህ፤  አንዳንዶች ኅሊናን ጥለው መርከብ ያለ መሪ እንደሚጠፋ በእምነት ነገር ጠፍተዋልና›› (፩ኛ ጢሞ.፩፥፲፱) መርከብ ያለመሪ በባሕር ላይ ቢጓዝ ዕጣ ፈንታው ከጥልቁ ሰጥሞ መጥፋት ነው፡፡

ሰዎች በተስፋ ከመቁረጥ የተነሣ ኅሊናቸውን ሲጥሉ፣ ማገናዘብ ሲያቁሞ፣ ሰብእናቸውን አጥተው፣ ከሕገ እግዚአብሔርም ወጠተው እንደሚጠፋ እንስሳት ሆነው በራሳቸው ላይ በሚወስዱት ያልተገባ እርምጃ፣ በምድር ኑሮአቸው ጨልሞ፣ ከሞት በኋላ ባለው ሕይወታቸውም ዕጣ ፈንታቸው ከዲያብሎስና ሠራዊቱ ጋር እሳቱ ከማይጠፋ ትሉ ከማያቀላፋ ዘለዓለማዊ እሳት ይሆናል፡፡ የዚህ ሁሉ ምክንያቱ በእምነት ነገር መጥፋት ነው፡፡ እምነት ከሌለ ተስፋ አይኖረውም፤ ተስፋ ከሌለው፣ በጎ ኅሊና አይኖረውም፤ ከጽድቅ ሳይሆን ከበደል፣ ከሕይወት ሳይሆን ከሞት ያደርሳል፡፡

ከጨለማው ባሻገር ብርሃን፣ ከአቀበቱ ጀርባ ለምለም ሜዳ፣ ከኀዘን ባሻገር ደስታ፣ ከወጀብና ከአውሎ ነፋስ በኋላ ጸጥታና መረጋጋት፣ ከትንሣኤ በኋላ ሕይወት እንዳለ የሚያምን ክርስቲያን፣ የሚገጥመውን ፈተና፣ መከራና ስደት፣ ማጣት፣ መገፋትን በአኮቴት ተቀብሎ፣ ነገን እያለመ በትዕግሥት ይጠብቃል፤ ምክንያቱም እግዚአብሔርን አምነው የሚያደርጓት ተሰፋ እንደማይጨበጥ ደመና (ጉም) አልያም ርቆ እንደተሰቀለ ዳቦ ሳይሆን፣ የሚፈጸም፣ እውነት የሆነ ነው፡፡ በእርሱ ዘንድ ያለን ተስፋ ምኞትና ናፍቆት ብቻ ሳይሆን አለኝታና መተማመን የሚገኝበት ነውና። ነቢዩ ዕንባቆም በመከራ ጊዜ እንኳን ቢሆን ጸንቶ መገኘት እንደሚገባ እንዲህ በማለት የገለጸው ለዚህም ነው፤ ‹‹….ምንም እንኳ በለስም ባታፈራ፣ በወይንም ሐረግ ፍሬ ባይገኝ፣ የወይራ ሥር ቢጎድል፣ እርሾችም መብልን ባይሰጡ፣ በጎችም ከበረት ቢጠፉ፣ ላሞችም በጋጣ ውስጥ ባይገኙ እኔ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይለኛል፤ በመድኃኒቴ አምላክ ሐሤት አደርጋለው፡፡››  (ዕን.፫፥፲፯)

በእግዚአብሔር ላይ እምነታቸው የጸና፣ ተስፋቸው የለመለሙ፣ ኅሊናቸው ሳይሞትባቸው የፈለጉትን አግኝተዋል፤ ከገቡበት ስምጥ፣ ከሰጠሙበት አዘቅት፣ ወጥተዋል፤ ከከበባቸው ጨለማ፣ ከወረደባቸው የመከራ ዶፍ፣ በመንገዳቸው የገጠማቸው ጉድባ ተሻግረዋል፤ በጉዟቸው የተጋረጠውን ወጀብ ተስፋን ይዘው፣ ከኅሊና ሞት አምልጠው ካሰቡበት ደርሰዋል፤ የሻቱትን አግኝተዋል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ብሎ እንደተጻፈ፤ ‹‹የሁሉ ዐይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፤ አንተም ምግባቸውን ትሰጣቸዋለህ››  (መዝ.፻፵፬፥፲፭)‹‹…በሁሉ እንገፋለን እንጂ አንጨነቅም፤ እናመነታለን እንጂ ተስፋ አንቆርጥም…፡፡›› (፪ኛ ቆሮ.፬፥፰)

እስራኤላውያን በግብጽ ከነበሩበት የሰቆቃ፣ የባርነት ሕይወት እግዚአብሔር በሊቀ ነቢያት መሪነት አውጥቷቸው ወደ ተስፋይቱ አገር ከነዓን ይጓዙ በነበረበጽት ጊዜ በኤርትራ ባሕር በፊሀሒሮት በሚባል ሥፍራ በነበሩበት ጊዜ ልበ ደንዳናው ፈርዖን፣ ማርኮ ዳግመኛ በባርነት ሕዝቡን ለመገዛት በማሰብ ሠራዊቱን አስከትሎ መጣ፤ እስራኤላውያን ከፊታቸው የኤርትራ ባሕር ተጋረጠ፤ ከኋላቸው የፈርዖን ሠራዊት ተከተለ፤ እምነታቸው ላልቶ በግብጻውያን ያደረገውን ድንቅ ሥራውን ረስተው ተስፋ ቆረጡ፤ ‹‹…በበረሃ ከምንሞት ብንገዛላቸው ይሻላል…››  እስከማለት ደረሱ፤ ሊቀ ነቢያት ሙሴ እምነቱ የጸና፣ በእግዚአብሔር ያለው ተስፋው የታመነ ነበርና አንደበቱን ሞልቶ ሕዝቡን እንዲህ አላቸው፤ ‹‹…አትፍሩ! ዛሬ የምታዩአቸውን ግብጻውያን ለዘለዓለም አታይዋቸውምና ቁሙ፤ ዛሬ ለእናንተ የሚያደርገውን እግዚአብሔርን ማዳን እዩ፡፡›› (ዘጸ.፲፬፥፲፫)

ሊቃውንት ሲያስተምሩ በእግዚአብሔር ለታመነው ለሊቀ ነቢያት ሙሴ በኤርትራ ባሕር መሐል የመጓዢያ ለምለም መስክ በእምነት መነጽር ይታየው ነበር፤ በእግዚአብሔር የሚታመን በድቅድቅ ጨለማ መሐል ብርሃን፣ ከከበቡት ተራሮች ባሻገር ለምለም መስክ ይታየዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ዘመነ ሰማዕታት ተብሎ በሚታወቀው የመከራ ዘመን ክርስቲያኖች አምልኮታቸውን በነጻነት መፈጸም፣ በዓላቸውን በደስታ በአደባባይ ማክበር ባልቻሉበት የጭንቅ ወቅት ተስፋ ሳይቆርጡ በግበበ ምድር (በካታኮም) መልእክታትን በኮድ  (በምሥጢር) በመጻፍ  በሰው ሰውኛ አይቻልም የተባለውን የመከራ ዘመን አልፈው፤ ለተከታይ ትውልድ ደማቸው ዘር፣ አጽማቸው አጥር (ከለላ)፣ ሆኖ ጠፉ ሲባል እየበዙ፣ ሞቱ ሲባል እየተኩ ክርስትናን አስቀጥለዋል፡፡

ክርስትና በደስታ ጊዜ የሚያምኑት ብቻ ሳይሆን በመከራ ጊዜ በሕይወት የሚገልጡት ነው፤ ታዲያ ይህን ለማድረግ ከኅሊና ሞት መጠበቅ ያሻል፤ ከኅሊና ሞት ለመዳን ደግሞ እምነት፣ ተስፋና ፍቅርን መያዝ ግድ ይላል፡፡

በአንድ ወቅት እንዲህ ሆነ፤ የሶርያው ንጉሥ ወልደ አዴር ሠራዊቱን ሰብስቦ ሰማርያን ከበባት፤ የሚገባም የሚወጣም ጠፋ፤ በሰማርያ ታላቅ ረኃብ ሆነ፤  ሰው የሚበላው ጠፍቶ የርግብ ኩስ  እስኪመገቡ ደረሱ፤ ከዚያም  የከፋ ነገርን አደረጉ! እግዚአብሔር ሕዝቡን ይታደግ ዘንድ በነቢዩ ኤልሳዕ አማካኝነት ረኀባቸው እንደሚወገድ መልእክት ለንጉሡ ተነገረው፤ ንጉሡ ኢዮራም ግን ከነበረው ረኃብ ጽናት የተነሣ ተስፋ ቆርጦ ነበርና ‹‹እግዚአብሔር በሰማይ መስኮቶች ቢያደርግ ይህ ነገር ይሆናልን..›› በማለት የተስፋ መቁረጥ እምነት መጉደል ያለበትን ንግግር ተናገር! (፪ኛ ነገ.፮፥፳፭)

ነቢዩ ኤልሳዕም ‹‹…እነሆ በዓይኖችህ ታየዋለህ፤ ከዚያም አትቀምስም አለ…›› (፪ኛ ነገሥ. ፯፥፩-፮) ነቢዩ ኤልሳዕ እንደተናገረው ሆነ እግዚአብሔር ይችላል፤ በአራት ለምጻሞች አማካኝነት ሶርያውያንን አስደንብሮ ከከተማው በራፍ እንዲሸሽ አደረገ፤ ሕዝቡም ያጣውን መብል (እህል) ከከበቧቸው ጠላቶቻቸው ሰፈር አግንቶ ተመገቡ፡፡ ሶርያውያን የጦር ሰፈራቸውን ለቀው መሄዳቸውን የሰማው ንጉሥ ሊመለከት ሲወጣ ሕዝቡ ገፍትሮ ጣለው፤ ረግጠውትም ሞተ፤ የእግዚአብሔር ነቢይ ኤልሳዕ ‹‹…እነሆ በዓይኖችህ ታየዋለህ፤ ከዚያም አትቀምስም …›› ብሎ እንደተናገረው እግዚአብሔር ለሕዝቡ ምግብን ሰጠ፤ ተመገቡም፤ ንጉሡም ተመለከተ፤ ግን አልተመገበውም፤  ምክንያም አስቀድሞ በኅሊናው ሞቷልና፡፡

አንዳንድ ጊዜ ነገሮች ሁሉ ሲቆላለፉ ሊሆን የሚችለው የማይሆን መስሎ ይታየንና ከማስተዋል ማነስና፣ ከእምነት መጉደል የተነሣ እንዴት ይሆናል? በሚል ሥጋዌ አመለካከትና እሳቤ የተስፋ መቁረጥ ንግግር ከአንደበታችን ይደመጣል፤ የኅሊናን ሞት ቀድመን እንሞታለን፤ እግዚአብሔር ግን ይችላል፡፡ የእኛ ኃላፊነት በማንኛውም ነገር በምንችለው መጠን ያቅማችንን ማድረግ ከዚያም እንደ ካህኑ ዔሊ ‹‹…እርሱ እግዚአብሔር ነው፤ ደስ ያሰኘውን ያድርግ…›› ልንል ይገባል፡፡ (፩ኛ ሳሙ.፫፥፲፰) እግዚአብሔር በአራት ለምጻሞች፣ ሰዎች በናቋቸው፣ ከማኅበረሰቡ በተገለሉ ሰዎች አማካኝነት ጠላቶቻቸውን አሳዶ የሕዝቡን ታሪክ ለወጠው፤ በእግዚአብሔር ከታመንን ሁሉን ማድረግ ስለሚቻል በአንዳች ነገር ተስፋን አንቆርጥም፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

የፍቅር ምርኮዎች

ታኅሣሥ ፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ፍጹም በሆነ ልዩ የልብ ስሜትና ኃይል ከራስ በላይ ለሌላ የሚኖር ደስ የሚያሰኝ መንፈስ፣ በሥቃይ ውስጥ የሚገኝ፣ እጅግ አስደናቂ ተፈጥሮ “ፍቅር ነው!” ፍቅር ሁለመናውን ይሰጣል፤ እንደራሱ ይወዳል፤ ለወደደው ያስባል፤ ይንገላታል፤ ይሠቃያል፤ ይሞታል፡፡

የፍቅር ባለቤት ጌታ ነው፤ በፍጹም ፍቅሩ ለሰው ልጆች ባሕይሪውን ዝቅ ያደረገ፣ ፈጣሪ ሆኖ ሳለ በሰዎች መካከል የተመላለሰ፣ እንደ ወንጀለኛ ተቆጥሮ በፍርድ ሸንጎ የቀረበ፣ የተከሰሰ፣ የተንገላታ፣ ጽኑ መከራን የተቀበለ፣ በሥቃይ ተሰቅሎ የሞተው አንዱ ጌታ ለፍቅር ነውና!

ድንቅ በሆነው ፍቅሩ ስቦ ተገዚዎቹ ያደረጋቸው የፍቅር ምርኮዎች ለፍቅር የሞተውን ጌታ በፍጹም ልባቸው፣ በፍጹም ነፍሳቸው፣ በፍጹም ኃይላቸው ወደዋል፡፡ (ማቴ.፳፪፥፴፯) ከራሳቸውም አልፎ ሰውን በፍጹም ልባቸው በመውደድ እጅጉን በሆነ ብዙ ሥቃይ እርሱን መስለው ተገኝተዋል፡፡ እውነትን ወደው ሐሰትን ጠልተዋልና፤ ከምድር ተድላ ይልቅ ሥጋዊ መከራን ፈቅደዋልና፤ ለፍቅር ሲሉ ተርበዋልና፤ ተጠምተዋልና፤ ተራቁተዋልና፤ ተሰደዋልና፤ ተንገላትተዋልና፤ ተሠቃይተዋልና፤ በግፍ ተድገለዋለና የፍቅር ምርኮዎች በመጨረሻ ያበራሉ!

ጸአር፣ ገአርና ኀሣር በሞላበት በዚች ጨለማ ዓለም፣ የምድራዊ ከንቱነት ታክቷቸው፣ ብርሃን የሆነውን ወንጌል በተስፋ ሰንቀው በጽድቁ ጎዳና በሚጓዙበት ጊዜ የሚመጣባቸውን ሥቃይ ስለ ፍቅሩ የሚቀበሉ ቅዱሳን በነጻ ፈቃዳቸው ለጌታ የሚገዙ የፍቅር ምርኮዎች ናቸው፡፡ በክርስቶስ ፍቅር የተንገበገቡ፣ ልባቸው የተቃጠለ፣ አንጀታቸው የተንሰፈሰፈ አፍቃሪዎቹ ናቸው፡፡

ዕለት ዕለት ስለ እርሱ ይገፋሉ፤ እውነትን ስለመሻታቸው ስደት ልማዳቸው ነው፤ ከሐድዲያንን ጠልተው ጽድቅን ይራባሉ፤ ቀን በበረኃ ውእየት፣ ማታ በጨለማ ቁር ይሠቃያሉ፡፡ በዱር ገደል መሽገው ዘወትር አምላካቸውን ያገለግላሉ፡፡ ይህን ሁሉ ስለ ጌታ ፍቅር አደረጉት!

ፍቅር እውነት በመሆኑም የእውነት ምስክሮች ሆኑ፤ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ‹‹ሰማዕታት የዚህችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ፡፡ ስለ እግዚአብሔር ደማቸውን አፈሰሱ፡፡ ስለ መንግሥተ ሰማያትም መራራ ሞትን ታገሡ›› በማለት እንደተናገረው ክሕደትና ሐሰት፣ ስርቆትና ንጥቂያ፣ ማስመሰልና ከንቱነት በበዛበት በዚች ውጥንቅጥ ዓለም ውስጥ ሲኖሩ፣ ሲገፉና ሲበደሉ ትዕግሥትን ገንዘብ አድርገው፣ በጽናት በጨለማ ውስጥ እንደ ሻማ አበሩ፡፡  (ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ) በዋሻ ሆኖ እንደሚለኮስ ጧፍ፣ በድቅድቅ ጉድጓድ ውስጥ እንዳለ ፋኖስ፣ በጠባብና ትንሽ ደሳሳ ጎጆ እንደሚያበራ መብራት ሆነው ደመቁ፡፡

ቀጥተኛ በሆነችው አንዲት ርትዕት ሃይማኖት፣ ለአንድ እውነተኛ አምላክ የመገዛታቸው ምስክር የክርስቶስን መከራ መስቀልም ስለ መሸከማቸው፣ ብርሃን የሆነው ጌታ በላያቸው ያበራል፡፡ ሕይወታቸው በሙሉ እርሱን በመፍራትና በመታዘዝ፣ ስለ ፍቅሩ ሲሉ ራሳቸውን ጥለው፣ ቤተ ሰቦቻቸውን ትተው፣ ቀያቸውን ለቀው፣ በስደትና በእንግልት መኖርን ስለፈቀዱ ብርሃን የሆነው አምላክ አይለያቸውምና፡፡

መላ ቅጡ በጠፋባት በዚህች መራራ ዓለም እንደ ጨው ሆነው ያጣፍጣሉ፡፡ ሐሰተኝነት ሲበዛ እውነት እንዳይጠፋ፣ ፍርድ ሲጓደል ፍትሕ እንዳይረሳ፣ ጥላቻ በሕዝብ መካከል ሲሠርጽ ፍቅር እንዳይጠፋ ምስክሮች ይሆናሉ፡፡ ስለት ሳያስፈራቸው፣ የጥፋት ሰንሰለት ሳያስራቸው፣ ሥቃይ ሳይበግራቸው ከጠላት ጋር ፊት ለፊት ተጋፍጠው እውነተኛ ስለሆነው ፈጣሪ መስክረዋል፤ ከፍቅሩም የተነሣ ጽኑ ግርፋትን ተቀብለዋል፤ ቆዳቸውን ተገፈዋል፤ በብረት መጋዝ ተቆርጠዋል፤ በፍል ውኃ ተቀቅለዋል፤ በእሳት ተቃጥለዋል፤ ‹‹….እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ሌሎችም መዘባበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ›› እንዲል፡፡ (ዕብ.፲፩፥፴፭)

ዘወትርም ቀራንዮን በማሰብ የጌታን ሥቃይ በእምነት መነጽር እየተመለከቱ በሚያቃጥል እንባ ልቅሶን ያበዛሉ፤ የተገረፈውን ግርፋት በማሰብ ጀርባቸውን ተገርፈዋል፤ ፊታቸውን በጥፊ ጸፍተዋል፤ ከፍቅሩ ብዛት ራሳቸውን ከቆጥና ዛፍ፣ ከድንጋይም ራሳቸውን ወርውረዋል፤  ሞተዋል፡፡ ድንቅ በመሆነው ተአምራቱ እርሱ ደግሞ ያስነሣቸዋል፤ ይፈውሳቸዋልም፡፡ (ገድለ አቡነ አቢብ)

የፍቅር ምርኮዎች የፍቅር ተገዢዎች ስለመሆናቸው በበጎ ፈቃዳቸው በነጻነት ለሚገዛ አምላክ በፍጹም ፍቅር አምልኮት ይፈጽማሉ፤ ኑሮአቸውም ሆነ ውሎአቸው፣ በፍሪሃ እግዚአብሔር መኖርን ይመርጣሉ፡፡ እርሱ መመኪያቸው ነውና ስለምንም ምን አይጨነቁም፤ አይፈሩምም፡፡ ጋሻ መከታቸው፣ ኃይል ብርታታቸው፣ ጽናት ተጋደሎአቸው አንድ ፈጣሪ ነውና፡፡ ልብሳቸውም ይሁን ምግብ መጠጣቸው እርሱ ነውና፡፡

በችግር ጊዜም ቢሆን መሻገሪያ ድልድያቸው፣ በመራቆት ሰዓት የጽድቅ ልብሳቸው፣ በመራብ ጊዜ ምግባቸው እርሱ ነው፡፡ የዘለዓለማዊ መብልና መጠጥን የሚያድል ኤልሻዳይ አምላክ የመሆኑን ምሥጢር በሚገባ የተረዱ ናቸውና ስለ ሥጋዊ መራብና መጠማት አይጨነቁም፡፡ እውነተኛ ሕይወትን የሚሰጥ ጌታ ለዘለዓለም በፍቅሩ ጠብቆ በሰላምና በነጻነት እንደሚያኖራቸው ፍጹም እምነት ያላቸው በመሆናቸው ሰማይና ምድር ለፈጠረ አንድ አምላክ ተገዝተው መኖርን የመረጡ ናቸው፡፡ በመጨረሻም ስለ ፍቅሩ በመሞት፣ መንግሥቱን በመውረስ ለዘዓለም ከእርሱ ጋር በተድላ ደስታ ይኖራሉ፡፡

የሰማዕታት የቅዱሳን ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ በረከታቸው ይደረብን፤ አሜን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

በአታ ለእግዝእትነ ውስተ ቤተ መቅደስ

ከደጋጎቹ ቅዱሳን አባቷና እናቷ ኢያቄምና ሐና የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ቀን የከበረ ነው፡፡ በበጎ ምክር በእግዚአብሐርም ፈቃድ ይህ ሆነ፤ በዚያን ጊዜ ኢያቄምና ሐና “….ሆዷ ዘመድ ሳይወድ አፏ እህል ሳይለምድ ወስደን እንስጥ” ብለው በመማከር መባዕም ጨምረው ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ፡፡   

ተዝካረ ልደቱ ለኤልያስ ነቢይ

ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ቅዱሳት መጻሕፍት ነቢዩ ኤልያስ የተወለደው በታኅሣሥ ፩ ቀን ከነገደ ሌዊ እንደሆነ ይገልጻሉ፤ የአባቱ ስም ኢያስንዩ የእናቱ ስም ቶና ይባላሉ፡፡ በተቀደሰች የልደት ቀኑም አባቱ ብርሃን የለበሱ አራት ሰዎች ሲሰግዱለትና ሕፃናት በሚጠቀልሉበት ጨርቅ ፈንታ በእሳት ሲጠቅልሉት  ተመልክቷል፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ዘኅዳር ፩፣ መዝገበ ታሪክ ገጽ ፹፬)

ኢትዮጵያ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተአምኆ ቅዱሳን መጽሐፉ ስለዚሁ ነቢይ እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ “ቴስቢያዊ (የቴስቢያ ሰው)፤ ኮሬባዊ (ወደ ኮሬብ ተራራ የወጣ)፣ ታቦራዊ (በታቦር ተራራ የተገኘ)፣ ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን የለጐመ ለሆነ፣ የጸሎቱ ቃልም በአዶናይ ዦሮ ውስጥ ለተሰማ፣ ውኃውን እስኪበላ ደርሶ እሳትን ከሰማይ ያወረደ ለሆነ፣ በእሳት ሠረገላ ተጭኖ ወደ ተድላ ደስታ ቦታ ለገባ ለነቢዩ ለኤልያስ ሰላምታ ይገባል።”

ሊቁ አርከ ሥሉስም በአርኬ መጽሐፉ ላይ ደግሞ እንዲህ ብሏል፤ “ምድራዊ የሆነ የዓለም ሕይወትን አራግፈህ ለማረፍ ወደ ሰማያት ያረግህ ለሆንክ ለአንተ ለኤልያስ ሰላም እላለሁ፡፡ አክአብን ለተናቀ ሥራው እየዘለፍከው ጣዖታትን የቀጠቀጥክ ማምለኪያዎቹን ያፈረስክ በምስጋናህ ምንኛ ተመሰገንህ።”

ቅዱሱ መጽሐፍ የዚህን ፈፍ  ነቢይ ስም “ኤልያስ” ፻ (መቶ) ጊዜ ጠቅሶታል፡፡ ድንቃ ድንቅ ተአምራቱንም መዝቦት እናገኛለን፤ ከእነዚህም መካከል አክአብና ኤልዛቤል ጣዖት በማምለከታቸው ኤልያስ ሦስት ዓመት ከ ስድስት ወር ዝናብን በጸሎቱ አቁሟል፡፡ (፩ኛ ነገ. ፲፯)፤ የሰራጵታዋን መበለት የሞተ ልጇን አስነሥቷል፡፡ (፩ኛ ነገ.፲፯፥፲፱)

ለአምላካችን እግዚአብሔር ያቀረበውን መሥዋዕት እሳት ከሰማይ ወርዶ የበላለት ነቢይ እንደሆነም መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፤ (፩ኛ ነገ ፲፰) ከሦስት ዓመት ከስድስት ወር በኋላ ቀርሜሎስ ወጥቶ በመጸለይ ዝናብ እንዲዘንብ አድርጓል፤ (፩ኛ ነገ. ፲፰) አካዝያስ የላካቸውን ፶ (ኀምሳ) አለቃዎች እሳት ከሰማይ አውርዶ አቃጥሏል፤ (፪ኛ ነገ. ፩) በመጐናጸፊያው የዮርዳኖስን ወንዝ ከፍሏል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፬) በእሳት ሠረገላ በዐውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጥቷል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፩)፣ በደብረ ታቦር ጌታ ምሥጢረ መንግሥቱን ሲገልጽ ከሙሴ ጋር ዐብሮ ተገኝቷል፤ (ማቴ.፲፯፥፬) ዳግመኛ በመምጣት በሐሳዌ መሲሕ ጊዜ ሰማዕትነትን ይቀበላል፡፡ (ማቴ.፲፯፥፲፩)

የነቢዩ ኤልያስ በረከት ይደርብን!

 

ሥዕለ አድኅኖ

 ክፍል ሦስት

ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ 

ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁ? እንኳን ለጾመ ነቢያት (የገና ጾም) አደረሳችሁ! ይህ ጾም የሚጾመው አባቶቻችንን ነቢያት እግዚአብሔር በሰጠን ተስፋ በገባልን ቃል ኪዳን መሠረት ከሰማያት ወርዶ እንዲያድነን “አቤቱ ውረድ፤ ተወለድ፤ አድነን” እያሉ የጾሙት ጾም ነው፤ እኛ ደግሞ ከሰማያት ወርዶ፣ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ አድኖናል እያልን ውለታውን እያስታወስን እንጾመዋለን፡፡ ከሰባቱ የዐዋጅ አጽዋማት አንዱ ስለሆነ እኛም እንደ አቅማችን ልንጾመው ይገባል! መልካም!

ትምህርታችሁንም በርትታችሁ ተማሩ! የመንፈቀ ዓመቱ ፈተናም እየተቃረበ ነው፤ በደንብ በማጥናት ጥሩ ውጤት ማስመዝገብ አለባችሁ! በሰንበት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መማርን፣ማገልገልንም እንዳትረሱ።

ባለፈው ትምህርታችን ስለ ሥዕለ አድኅኖ በተማርነው ትምህርት ሥዕለ አድኅኖ እንዴት መሣል እንዳለበት በመጠኑ ተምረናል፡፡ ዛሬ ደግሞ ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል የምንጠቀማቸው ቀለማት (ከለር) ምን ዓይነት መሆን እንዳበቸውና ምክንያቱን የተወሰኑትን ለአብነት እንመለከታለን፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለቅዱሳት ሥዕላት የምንጠቀማቸውን የቀለማት ውክልና ከማየታችን በፊት ቀለም ምንድን ነው የሚለውን እንመልከት፤ ቀለም የሚለውን ሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ የቃላትን ፍቺ (ምሥጢር) በተረጎሙበት መጽሐፋቸው ቀለም በቁሙ “ኅብር፣ ፈሳሽ፣ ዓይነት፣ መጣፊያ፣ ማቅለሚያ” ብለው አብራርተውታል፡፡ (ኪዳነ ወልድ መዝገበ ቃላት ገጽ ፯፻፺፫/793)

ቀለማት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ሥዕለ አድኅኖ ሲሣሉ የሚያስተላልፉት መልእክትም አላቸው፤ የፈጣሬ ዓለማት የቅድስት ሥላሴ፣ የእመቤታችን ቅድስት ደንግል ማርያምን፣ ሥዕል ሲሣል የሚቀባው ቀለም ዓይነት የራሱ የሆነ ትርጒምና የሚያስተላልፈው ነገር አለው፤ የቅዱሳን መላእክትን፣ የቅዱሳን አበውን፣ የቅዱሳት እናቶችን ሥዕልም በሚሳልበት ጊዜ የተጋድሏቸውን ጽናት፣ የክብራቸውን ዓይነት፣ የመጠሪያ ስያሜአቸውን ለመለያነትም ያገለግላል፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! የቅዱሳን ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል በሥዕሉ ባለቤት በራሱ           ዙሪያ በክብ ቅርጽ ጸዳለ ብርሃን (አክሊለ ብርሃን) ተደርጎ ይሣላል፤ በዚህም ለመግለጽ የተፈለገው ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያን የቅድስና ማዕረግ እንደተሰጣቸው ለመግለጽ ነው፡፡

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ክቡ ቅርጽ በቅድስት ሥላሴና በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሥዕለ አድኅኖ ላይ የሚደረገው ጸዳለ ብርሃን የእግዚአብሔር ቅድስና የባሕርይው መሆኑን ለመግለጽ ነው፡፡ ለቅዱሳን ሲደረግ ደግሞ አምላካችን የባሕርይ ቅድስናውን መልካም በመሥራታቸው በጸጋ (በስጦታ) ለቅዱሳን ቅድስናን እንደሰጣቸው ለመግለጽ የቅዱሳት ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል በራሳቸው ዙሪያ በብርሃን ክብ ቅርጽ ይደረግላቸዋል፡፡

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! በቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና መሠረት አብዛኛውን ጊዜ የምንጠቀማቸው ቀለማት ነጭ፣ ሰማያዊ፣  ቢጫ፣ አረንጓዴና ቀይ ሲሆኑ ቀለማቱ ራሱን የቻለ ምሥጢር ወይም ትርጒም አላቸው፡፡

 ነጭ፡- የድል አድራጊነት፣ የንጽሕና እና የፍጹምነት ምሳሌ ነው፡፡ ቅዱሳን ዓለምንና ምኞቱን ድል ያደረጉ ልበ ንጹሐን በመሆናቸው ነጭ ልብስ ለብሰው ይሣላሉ፡፡ እንዲሁም ደግሞ መለኮታዊ ክብርንም ያሳያል፡፡ ለምሳሌ በደብረ ታቦርና በትንሣኤ ሥዕሎች ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነጭ ልብስ ለብሶ ይሣላል፡፡ (ኦርቶዶክሳዊ ቅዱሳት ሥዕላት ገጽ ፸፬)

ሰማያዊ፡- ሥዕለ አድኅኖ ሲሣሉ ሰማያዊ ቀለምን መቀባቱ በመልካም ሥራው ሰማያዊውን ሀብት (መንግሥተ ሰማያትን) ገንዘብ ለማድረግ (ለመውረስ) አባቶቻችን ቅዱሳን በፈቃደ ነፍስ ለመመራት መልካም ሥራን ለመሥራታቸው፣ ኃጢአትን መጥላታቸውን ለሰዎች መልካምን ማድረጋቸውን ለማመልከት እንዲሁም በመንፈስ ፍሬዎች በተባሉ በትዕግሥት፣ በትሕትና፣በፍቅር፣ በደስታ፣ በእምነት፣ በቸርነት (ገላ. ፭፥፳፪) ፈቃደ ሥጋን (ክፉ ምኞቶችን ሁሉ ድል ማድረጋቸውን ለማመልከት ለሥዕለ አድኅኖ ሲሣሉ ይህንን ቀለም እንጠቀመዋለን፡፡ሌላው ደግሞ ከቁጣ፣ ከቂም፣ ከበቀል ርቀው በትሕትናን ለመኖራቸው ምሳሌ ነው፡፡

 ቢጫ፡- ይህ ቀለም እውነተኛነትንና ብርሃንነትን ይገልጻል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትምህርቱ ‹‹እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ …›› (ማቴ.፭፥፲፬) በማለት እንዳስተማረው በመልካም ሥራቸው ለሌላው ብርሃን የሆኑትን ቤተ ክርስቲያን የቅድስና ማዕረግ ላይ የደረሱትን ቅዱሳን እውነተኞችና የዓለም ብርሃን ናችሁ ስትል በራሳቸው የብርሃን አክሊል በቢጫ አድርጋ ትሥላለች፡፡

አረንጓዴ፡- ከልምላሜና ከጸዳል ጋር ስለሚያያዝ መንፈሳዊ ትርጒሙ መታደስን አዲስ ሕይወት፣ ደኅንነትና ተስፋን ያሳያል፡፡ በዚህ መሠረት በትንሣኤ በአዲስ ሕይወት እንደምንኖር ያመለክትልናል፤ አረንጓዴነትና ሕይወት ተወራራሽ ይሆናሉ፡፡

 ቀይ፡- ሥዕለ አድኅኖ  ሲሣሉ በቀይ ቀለም መሳላቸው ሰማዕትነትን ያሳያል፤ ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውያን ምእመናን በላከወ መልእክቱ ‹‹…በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፣ ተፈተኑ በመጋዝ ተሰነጠቁ፣ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ …›› (ዕብ.፲፩፥፴፮) በማለት እንደገለጸው ስለ ሃይማኖታቸው መከራ የተቀበሉትን ሰማዕት የሆኑትን ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን ሥዕለ አድኅኗቸው በቀይ ቀለም ይሣላል፤ ቅዱሳን ነፍሳቸውን ለመከራና ለሞት አሳልፈው ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርስቲያን ብለው መስጠታቸውን ለማመልከት ይህንን ቀለም እንጠቀመዋለን፤ እንዲሁም ቀይ ቀለም የነጻ አውጪዎችም ምልክት ተደርጎ ይወሰዳል፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለዛሬ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሐዶ ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል ምንን ዓይነት ቀለማት እንደምንጠቀም በመጠኑ ለአብነት ተመልክተናል፤ በቀጣይ በሥዕለ አድኅኖ የተደረጉ ተአምራት እንማራለን፤

ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ በዘመናዊ ትምህርታችሁ በርትታችሁ ተማሩ ለወላጅ መታዘዝን፣ ለሰዎች መልካም ማድረግን እንዳትረሱ፤ በሰንበት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መንፈሳዊ ትምህርትንም ተማሩ፡፡ ቸር ይግጠመን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

 

ትሩፋን

ኀዳር ፳፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 ቅዱሱ መጽሐፍ ትሩፋን ከጦርነት፣ ከስደት፣ ከምርኮ የተረፉትን ሰዎች እንደሚያመልክት ይነግረናል፡፡ “ትሩፍ” ጥሬ ቃሉ “የቀረ፣ የተረፈ፣ ቀሪ፣ ትርፍ” የሚል ትርጓሜ አለው፡፡ (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ፣ ገጽ ፱፻፫) ናቡከደነፆር እስራኤልን ወደ ባቢሎን ማርኮ ከወሰዳቸው ከሰባ ዘመን በኋላ በባቢሎን የቀሩት ከተማረኩት ሽማግሎች ትሩፋን ይባላሉ። በንጉሡ ዘመነ መንግሥት ከኢየሩሳሌም ተማርከው ሰባ ዘመን በፋርስ በባቢሎን የሚኖሩ የእስራኤል ሕዝብ ትሩፋነ ባቢሎን እንደሆኑም መጽሐፍ ያስረዳናል። (ዕዝራ ፪፥፩)

በተለያዩ ዘመናት በአንድም በሌላ ምክንያት በሰዎች፣ በጎሳ፣ በማኅበረሰብ ዘንድ እንዲሁም በሀገራት መካከል በሚከሰት ጦርነት እልቂት አልያም የግፍ ግድያና ጭፍጨፋ የተነሣ የብዙዎች ሕይወት ይጠፋል፤ ታሪክ ለዚህ ቀደምት ምስክር እንደሆነ የምናውቀው እውነት ነው፡፡ የጦርነት ወሬ ደግሞ ለእኛ አዲስ የሆነ ነገር አይደለም፡፡ እራሱ ጌታ በወንጌል ሲናገር  ‹‹ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፤ አትደንግጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው። ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣልና፥ ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል›› እንዳለው ምድር ላይ እነዚህ ሁሉ መከራዎች እየተከሰቱ እንደሆነ ለማንም የተደበቀ አይደለም፡፡ (ማቴ.፳፬፥፮-፯)

ታዲያ የጦርነት አስከፊ ገጽታው እንጂ መልካም ጎኑ ምን አልባት እርሱ ባወቅና በፈቀደ ጠላትን ከሀገር የማስወጣቱ ተግባር ነው፡፡ በዚህም አብዛኛዎቻችን ጦርነትን በውዴታ ሳይሆን በግዴታ የምንቀበለው ነው፡፡ ከሁሉም አስከፊው ደግሞ ቤተሰቦቻቸውን፣ ዘመድ አዝማዳቸውንና ወዳጆቻቸውን የሚያጡ ትሩፋን የሚገጥማቸው ሥቃይና ጉዳት ነው፡፡ በአንድ በኩል ከአሰቃቂ ግድያ አልያም ከሞት መትረፍ ቢያስደስትም በሌላ በኩል ግን የሚወዱትን ማጣት እጅግ አስከፊ ነው፡፡ ከምንም በላይ ግን የሞት ሞት የሆነው የነፍስ ሞት አሰቃቂ ነው፡፡

ሰዎች ሞትን እንፈራለን፤ የሥጋ ሞት አስጨናቂ እንደሆነ ማንም የማይክደው ሐቅ ነው፡፡ ነገር ግን ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ኢትፍርህዎ ለሞት፤ ፍርህዋ ለኃጢአት፤ ሞትን አትፍሩ፤ ኃጢአትን እንጂ›› ይለናል፡፡ ሊያስጨንቀን የሚገባው በኃጢአት ምክንያት የሚመጣብንን የነፍሳችን ሞት እንጂ የሥጋ ሞት ሊሆን እንደማይገባ በዚህ ቃል እንረዳለን፡፡ ‹‹አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ›› በሚለው አምላካዊ ቃል ሥጋዊ ሞት አይቀሬ በመሆኑም ምንም ለማንቀይረው  ነገር መጨነቁ ጥቅም የለውም፡፡ (ዘፍ.፫፥፲፱) 

የነፍስ እንጂ የሥጋ ጦርነት ትሩፋን ባንሆን እጅጉን ይመረጣል፡፡ ቃሉን ተረድተው፣ በሕጉ ኖረው ትእዛዙን የጠበቁ ጻድቃን ሁሉ በነፍሳቸው አትርፈው ከዚህ ዓለም ድካምና ዕረፍት በክብር እንደተለዩ ቅዱሳት መጻሕፍት ምስክር ናቸው፡፡ (ገድለ ቅዱሳን) አብነት መሆናቸውን ደግሞ በክርስቶስ ክርስቲያን የተባልን የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ሁላችን ማወቅ አለብን፡፡   እውነት ስለሆነው አንድ ጌታና አንዲት እውነተኛ ሃይማኖት ሲሉ መከራን በመቀበል በቀናው መንገድ ተጉዘው መልካም ፍሬን ያፈሩ ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት የነፍስ አትራፊዎች/ትሩፋን/ ናቸው፡፡

የልባችን መሻት የሁላችንም ምኞት መሆን ያለበት ይህ ነገር ሆኖ ሳለ፣ በመንፈስ ውጊያ ለማሸነፍ የሚያስችለንን ስንቃችንን ደግሞ ማከማቸት አስፈላጊ በሆነበት ሰዓት፣ እኛ ግን እየተጨነቅን ያለነው በጊዜያዊ ችግርና ወቅታዊ የእርስ በርስ ጦርነት ላለመሞት ነው፡፡ የሥጋዊ ሞትን ፈርተን በምንዘናጋበት ጊዜ ግን ነፍሳችንን እንደ አንበሳ ነጥቀው ሊጥሏት ይችላሉና ይህንን እንፍራ!

ነፍስ ዘለዓለማዊ ስትሆን ሥጋ ግን ጊዜያዊ ነው፤ አላፊ ጠፊ የሆኑ ምድራዊ ነገሮችን ለሟሟላት በሚል በምድር ለመኖር ስንሻ ከሁለት ያጣም የመሆን ሁኔታ ሊኖር ስለሚችል መጠንቀቅ ይገባል፡፡ ስለ ሥጋዊ ሞት ስናስብ መንፈሳዊ ዝለት ያጋጥመናል፤ በዚህም ጊዜ ነፍሳችን ትጎዳለች፤ ታድፋለች፤ ትመነምናለች፡፡

ሰው ጦርነትን ፈርቶ ሊሸሽ ይችላል፤ መሰደደም ሆነ መደበቅም አይከፋም፤ ግን ግልጽ የሆነውን አስከፊ ሁኔታና እየተካሄደ ያለውን ጦርነትም ይሁን እልቂት ማስቆም ካልተቻለ ሃይማኖታችን በሚፈቅድልን ተገቢ መንገድ ድምጻችንን ማሰማቱና መልእክት ማስተላለፍ እንጂ የጠላት ወገን ከሆኑ አካላት ጋር ግብ ግብ መፍጠር አልያም ጦርነት ውስጥ መግባት አላስፈላጊ ነው፡፡ ጠላት ፊት ለፊት መጥቶ ሊገለን ቢፈልግ እንኳን “ማኅተባችንን አንበጥስም” ብለን አንገታችንን ለሰይፍ ሰውነታችንን ለሞት አሳልፈን መስጠት ሰማዕትነት ነው፤ የክብር ሞትም ያሰጠናል፡፡

በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተለይም በዕረፍት በዓሏ በየወሩ ፳፩ ቀን የሚነበበው መልክአ ማርያም ‹‹ኃጥአን ከታላቅ የደስታ አደባባይ በተሰደዱ ጊዜ ምርኮ እሆንሽ ዘንድ ከእነርሱ ለይተሽ አስቀሪኝ›› ይለናል፡፡ (መልክአ ማርያም) ይህ ድንቅ ጸሎት የሚያመለክተን ከጦርነት ምርኮኝነት ለማምለጥ ማቀድ ሳይሆን ከኃጥአን ጎራ ላለመቆጠር መሻት እንዳለብን እንዲያውም የፍቅር ምርኮ መሆን እንደሚገባ ነው፡፡

ንጽሕት ቅድስት ከምትሆን የአምላክ እናት የተለመነው ይህ መማጸኛ ለሁላችን እንደሚሆን  እናምናለን፡፡ የነፍሳችንን ጥፋት የማይፈልገው አምላካችን አንዲያ ልጁን አሳልፎ ሰጥቶ ያዳነን ክብርት በሆነች እናቱ ድንግል ማርያም ነውና ታማልደን፣ ትለምንልን እና ትራዳን ዘንድ መማጸን የተገባን ነን፡፡ ከጠላት ሰይጣን የመንፈስ ውጊያ እንድታተርፈን፣ ምርኮዎቿ  እንድታደርገንን እንለምናት፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

አጠንተ መንበሩ!

ኀዳር ፳፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

አልፋና ኦሜጋ የሆነው አምላካችን ቅድመ ዓለም አስቀድሞ ሲለሠስ ሲቀደስ እንደኖረ ሁሉ ድኅረ ዓለም በፍጥረታቱ ሁሉ ሲመሰገን፣ ሲቀደስና ሲከበር ይኖራል፡፡ ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ የፈጠራቸው መላእክትና ሰውም ይህን ግብር የሚሠሩ ቀደምት ፍጥረታት ናቸው፡፡ (መጽሐፈ አክሲማሮስ ዘእሑድ)

የአምላካችን እግዚአብሔር ምስጋና በሰማይና በምድር ነው፤ በዓለመ መላእክት ዘወትር “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ” እያሉ ከሚያመሰግኑት መላእክት ሁሉ በላይ “አጠንተ መንበሩ” ተብለው የሚጠሩት “ካህናተ ሰማይ” ናቸው፡፡ በምድር ባለች ማኅደረ መለኮት የአምላክ ማደሪያ ቤተ ክርስቲያን ምድራዊ ካህናት በታቦቱ ፊት ማእጠንት እያጠኑ እንደሚያመሰግኑ ሁሉ፣ ቅዱሳን ሱራፌል ሃያ አራቱ ካህናትም የቅድስት ሥላሴን መንበር እያጠኑ ሳያቋርጡ ያመሰግናሉ፡፡

ነቢዩ ኢሳይያስም ስለ እነርሱ ሲናገር እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ንጉሥ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን በረዥምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀምጦ አየሁት፤ የልብሱም ዘርፍ መቅደሱን ሞልቶት ነበር። ሱራፌልም ከርሱ በላይ ቆመው ነበር፥ ለእያንዳንዱም ስድስት ክንፍ ነበረው፤ በሁለት ክንፍ ፊቱን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ እግሮቹን ይሸፍን ነበር፥ በሁለቱም ክንፍ ይበር ነበር። አንዱም ለአንዱ፦ ‘ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፣ ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች’ እያለ ይጮኽ ነበር።›› (ኢሳ.፮፥፩-፭) ቅዱስ ዮሐንስ ደግሞ ‹‹በዙፋኑ ዙሪያም ሃያ አራት ዙፋኖች ነበሩ፥ በዙፋኖቹም ላይ ነጭ ልብስ ለብሰው በራሳቸውም የወርቅ አክሊል ደፍተው ሃያ አራት ሽማግሌዎች ተቀምጠው ነበር›› ብሏል፡፡ (ራእይ ፬፥፬)

እነዚህ ቅዱሳን መላእክት ሱራፌል ሥጋ የሌላቸው ረቂቅ የእውነት ካህናት ናቸው፡፡ ከሰማያዊ ሠራዊት ሁሉ ከፍ ከፍም ይላሉ፡፡ የሰው ልጆችን ጸሎት፣ ምጽዋትንና ጽድቅን በልዑል እግዚአብሔር ፊት ያቀርባሉ፡፡ የሚጸለየውን ጸሎትና የሚሠዋውን መሥዋዕት በማዕጠንታቸው እያሳርጉ ሕያዋን ሆነው ይኖራሉ፤ አይሞቱም፤ አይለወጡም፡፡

በከበረች ኅዳር ፳፬ (ሃያ አራት) ቀን የስማቸው ትርጓሜ ሱራፌል “አጠንተ መንበሩ ለልዑል፣ ኤልሻዳይ” የሆነ ካህናተ ሰማይ የበዓላቸው መታሰቢያ ነው፤ አባታችን ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑበት ዕለት  ነው፡፡

የቅዱሳን መላአክት ሱራፌል፣ የቅዱሱ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ይደርብን!

ጽዮን ማርያም

ኀዳር ፲፱፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 ጽዮን “”ጸወን” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን “አምባ፣ መጠጊያ” ማለት ነው፡፡ እመ ብዙኀን የሆነችውን የአምላክ እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚገለጽ መሆኑን  “ማኅደረ አምላክ” በሚለው ትርጒም እንረዳለን፡፡ ጽዮን የሚለው ስያሜ በቁሙ ለታቦት፣ ለጽላት ሲያገለግል በትንቢታዊ ምሥጢሩ ግን ለድንግል ማርያም፣ ለቤተ ክርስቲያንና ለዘለዓለማዊት ርስተ መንግሥተ ሰማያት ያገለግላል::

ታቦተ ጽዮን “ጽላተ ኪዳን፣ ታቦተ ሕጉ” እየተባለችም ትጠራለች:: “ጽሌ” ማለት “ሰሌዳ” ማለት ሲሆን “ጽላት” ደግሞ በብዙ ቁጥር ነው:: “ኪዳን” ደግሞ በፈጣሪና በሰው ልጆች መካከል ያለ “ውል፣ ስምምነት” ነው፡፡ ታቦተ ጽዮን ዐሥርቱ ቃላት የተጻፈባት በመሆኗ የእግዚአብሔር ሕግጋትን የያዘ ናት፡፡ በዚህም በሕጉ እንድመራ ትእዛዙን እንድፈጽም ያሳስበናል፡፡

አልፋና ኦሜጋ፣ ኤልሻዳይ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር አስቀድሞ ለእስራኤል ሕዝብ ቅድስት የምትሆን ማደሪያውን ታቦተ ጽዮንን በነቢዩ ሙሴ አካማኝነት የሰጣቸው ክብር፣ ሞገስ፣ አምባ እንድትሆናቸው ነው፡፡ (ዘጸ. ፴፩፥፲፰)  ለ፭፻ (አምስት መቶ) ዓመት ከእነርሱ ሳትለይ ከአምላክ ጋር መገናኛ፣ በጦርነት ጊዜም ማሸነፊያ ኃይላቸው ሆናም ኖራለች፡፡

ሀገረ እግዚአብሔር የሆነችው ኢትዮጵያም ለከበረች ታቦተ ጽዮን መቀመጫ ለመሆን ታድላለች፡፡ በቀዳማዊው እብነ መለክ፣ እብነ ሐኪም/በቀዳማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት አማካኝነት ወደ ሀገራችን የመጣችው ታቦቷ እስከ አሁን ድረስ በአክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን እንደምትገኝ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይናገራሉ፡፡ (መጽሐፈ ክብረ ነገሥት) የጌታችን ድንቅ ቸርነት የተደረገልን እኛ የድንግል ማርያም የዐሥራት ልጆች የአምላክን ሥራ ልናደንቅና ልናመሰግን ይገባል፡፡

ሀገራችን የገባበትን እንዲሁም አክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን የተቀመጠበት ኅዳር ፳፩ ቀንንም ታላቅ በዓልን እናደርጋለን፡፡

የአምላካችን እግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ያሳትፈን፤ አሜን!

 

የተቀማ ማንነት

ኀዳር ፲፯፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

የማንነት ጥያቄ በሁላችንም አእምሮ ውስጥ የሚታሰብ ነው፤ ምላሽ አግኝተን የተሻለ መረዳት ያለን ስንቶቻችን እንደሆንን ማወቅ አዳጋች ቢሆንም በዘመናት ሂደት በሰዎች ታሪክ ውስጥ ካካበትነው ዕውቀት አልያም ደግሞ ባሳለፍነው ተሞክሮ የተወሰነ መረዳት ሊኖረን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡ በተለይም የአምላክን ቅዱስ ቃል ተምረን የምናውቅበት የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በመጠኑ እንኳን ካለን የመፈጠራችን ምክንያት ወይም የመኖራችን ትርጒም ይገባናል፡፡

ዓለምን ከእነጓዟ የፈጠረ ኤልሻዳይ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር በአርአያውና በአምሳሉ ሰዎችን ከሌሎች ፍጥረታት ለይቶ ሲፈጥረን  ስሙን እንድንቀድስና ክብሩን እንድንወርስ እንደሆነ ቅዱሱ መጽሐፍ አስቀድሞ ይነግረናል፡፡ (ዘፍ.፩፥፳፮) በዕፀ በለስ ምክንያት የሰው ዘር ያጣውን ልጅነት ሊመልስለት አንዱ እግዚአብሔር ወልድ ባሕርይውን ዝቅ አድርጎ፣ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከንጽሕት ድንግል ተወልዶ፣ መከራን ተቀብሎ፣ በመስቀል ተሰቅሎ የሞተልን፣ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ ብሉ ጠጡ ያለን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ የድኅነትን መንገድ የመሠረተልን መከራ መስቀሉን ተቀብለን በክርስቶስ ክርስቲያን እንድንሆን ነው፡፡

ቅዱስ ቃሉን አስተምሮ፣ በፈቃዱና በቸርነቱ የሰጠን እውነተኛዋ ሕይወት ክርስትና የማንነታችን መገለጫ መሆኗን ግን ተረድተን ይሆን? ‹‹እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ›› ያለን ጌታ እርሱ ክርስቶስ ተብሎ ክርስቲያን እንድንባል እንዳደረግን፣ በእውነተኛውም መንገድ መጓዝ እንዳለብን የተረዳን ስንቶቻችን እንሆን? (ዮሐ.፲፬፥፮)

የምድራዊ ሕይወት ባመጣብን ጣጣ፣ በድመክመታችን ሳቢያና በኃጢአታችን ብዛት ለጥፋት ተዳርገን፣ ቀና በሚመስለው ጎዳና አሳችና ጠማማ መንገድ እየተጓዝን ያለን፣ ማንነታችንን የተቀማን ሰዎች ጥቂት አይደለንምና ቆም ብለን ልናስብ ይገባል፡፡ አስቀድሞ ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ከፈጣሪያችን አጣልቶ ለ፶፻፭፻ (አምስት ሺህ አምስት መቶ) ዘመን ፍዳ አጽንቶ በኃጢአት ባርነት ገዝቶ እንዳሠቃየን ሁሉ ዛሬም አሳሳች በሆነችው ዓለም ጠፍተን እንድንቀር በተለያየ መንገድ ያጠምደናል፡፡ በጥቅም፣ በሀብት፣ በዝና የተደለሉት ወንድሞቻችን ዛሬ የት ናቸው? የዓለም ብልጭልጭ እያዋዛች ስባ፣ ጎትታ ጥላቸው፣ በርኩስ መንፈስ ተይዘው፣ በስካር ለዝሙት የተዳረጉ የዳንኪራ ቤት ደንበኞች የሆኑ ከእኛ የወጡ ኦርቶዶክሳውያንም ናቸው፡፡

“በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” እንዲሉ በኃጢአታችን ሳቢያ የአምላክ ቁጣ በላያችን በበረታበት በዚህ ጊዜ ምድራዊ ሕይወትን እንኳን ለመኖር አዳጋችና አሳሳቢ ደረጃ በደረሰበት ወቅት፣ ዛሬ እንሙት መቼ በማናውቅበት በአሁኑ ሰዓት ተስፋ አጥተን፣ ማንነታችን ተቀምተናልና እናስተውል! እንመለስ! የተቀማ ማንነታችን እናስመልስ!

ክርስትና ሕይወት ነው፤ እርሱ ክርስቶስ በሞቱ ሞትን አጥፍቶ እውነተኛ ሕይወትን ሰጥቶናልና፡፡ ተስፋ ነው፤ የመሠረታት አምላክ ነውና፡፡ ብርታትና ጽናት ነው፤ መከራ መስቀሉ ኃይልን ያደርጋልና፡፡ ‹‹መስቀል ኃይልነ›› እንዲል፡፡ (የዘወትር ጸሎት) ሥቃይና መከራ ችለን ፈተናችንን ማለፍ የሚቻለን፣ ዓለም የምታመጣብንን ሥቃይ መቋቋም፣ እስከ መጨረሻውም ልንጸና የምንችለው ክርስቶስ በተቀበለልን ጽኑ ሥቃይ በመስቀሉ ቤዛነት አምነን እርሱን ስንከተል እንጂ “ጦር መዛዥ ስለመጣ እኛም መሣሪያ ይዘን ጦርነት እንግጠም” ማለት ለማንም አይበጅም፤ ማንነታችንም አይደለም፡፡ ይህ ፍራቻ የፈጠረው የተሳሳተ አስተሳሰብና አካሄድ በመሆኑ “ጠላት ሲመጣ ዝም ብለን መሞት ሞኝነት ነው፤ ተዋግተን ማሸነፍ አምላክ የፈቀደው ነው” ብለን ለባሰ ጥፋት እንዳንዳረግ እንጠንቀቅ!

ይልቁንም ጠላትን ለማሸነፍ የሚያስችለንን ጥንተ ጠላት ዲያብሎስ የወሰድብንን የተቀማ ማንነታችንን “ክርስቲያናዊነታችንን” እናስመልስ፤ በእንደዚህ ዓይነት ወቅት ጦርነት ሲኖር ፍራቻ እንዲፈጠርብን ያደረገብን ያጣነው ማንነታችን ነው፤ ለሃይማኖት መሞት ክብር እንጂ ውርደት አይደለምና፡፡ የሰማዕትነትን ክብር ከታደሉ ቅዱሳን ጋር እንድቆጠር የሚያደርገን ክርስትናችንን ማጣት እጅጉን ያሳስባልና በጊዜ መመለስ ያስፈልጋል፡፡

ከምንም በላይ የንስሓ ልብ ይኑረን! ርኅራኄ አጥተን ለወገኖቻችን ምሕረትን ማድረግ ያልቻልን አካላት በሙሉ ትክክል የሆንን ሊመስለን ይችላል፡፡ ሆኖም ግን ነገሩ የተገላቢጦሽ ነው፡፡ በመልክም፣ በገጽም፣ በባሕርይም የሚመስለንን ፍጡር በአሰቃቂ ሁኔታ መጨፍጨፍ ወይም ለማጥፋት መፈለግ ማንንም አይጠቅምምና፡፡ የራስን ወንድም ወይም ወገን መግደል ምኑ ላይ ይሆን ጥቅሙ? ይህ ክርስቲያን ከሆንን ሰዎች አይጠበቅምና ልብ እናድርግ! ማንነታችን ስለተቀማን ደግሞ እንዘን!

በቁጭትና በመንፈሳዊ ቅንዓት ተነሣሥተንም እውነተኛ ማንነታችን እንፈልግ፤ እናስመልስ፤ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ለወገኑ ለጠላቱም ጭምር የሚጸልይ እንጂ ስለ ጎዳኝ ልጉዳው፣ ስለ መታኝ ልምታው፣ ስለ ተጠቀመብኝ ልጠቀምበት፣ ስለ ረገመኝ ልርገመው፣ ቤተሰቤን ስለ ገደለብኝ ልግደልበት አይልም፡፡ የሚያሣቃዩንንና በዳዮቻችንን መታገሥ፣ የሚረግሙንን መመረቅ፣ ለሚያሳዱዱን መጸለይ ለፍቅር የሞተልን፣ በቀራንዮ እንደ በግ እየተጎተተ፣ ጥፊንና ሕማማን እንዲሁም ግርፋትን ችሎ፣ እንዲያውም ለጠላቶቹ “አባት ሆይ፥ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” ብሎ የለመንንና የተሠዋልን ጌታ አስተምሮናል፡፡

በክፋት፣ በምቀኝነት፣ በክፉ ቅንዓት ምድር ላይ መርዝ ረጭቶ የበረዘን ጠላት ማንነታችን ቀምቶ ከፈጣሪ እንዳጣለን በማስተዋል የደኅነታችን መገኛ ወደ ሆነው፣ ክርስቶስ ተብሎ ክርስቲያን እንድባል ያደለን፣ የእውነተኛ ማንነታችን መገለጫ የሆነውን ክርስትናችን ወደ ሰጠን አምላካችን እንመለስ፡፡ ኃይላችን እርሱ ነውና፤ ማሸነፊያችን እርሱ ነውና፤ ተስፋችን እርሱ ነውና፤ ዘለዓለማዊ ሕይወትና ተድላ ደስታን የሚሰጠን እርሱ ነውና የተቀማ ማንነታችን እናስመልስ!

 

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

 

ነቢያት ለምን ጾሙ?

ኅዳር ፲፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

የአዳም ዘር በሙሉ በኃጢአት ባርነት ተይዞ፣ ለ፶፻፭፻ ዓመታት በፍዳ አረንቋ ውስጥ ሲኖር ተስፋ ሲያደርግ የነበረው የእግዚአብሔር አብ ልጅ እግዚአብሔር ወልድ ለአዳም የገባለትን የመዳን ቃል ኪዳን ነው፡፡ ይህም ይፈጸም ዘንድ ነቢያት አስቀድሞ ትንቢት ተናግረዋል፡፡

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስለ መወለዱ ፥ ወደ ግብፅ ስለ መሰደዱ ፥ በባሕረ ዮርዳኖስ ስለ መጠመቁ ፥ ብርሃን በሆነው ትምህርተ ወንጌል ጨለማውን ዓለም ስለ ማብራቱ ፥ ለሰው ልጆች ድኅነት ጸዋትወ መከራ ስለ መቀበሉና ስለ መሰቀሉ ፥ ስለ ትንሣኤው ፥ ስለ ዕርገቱና ስለ ዳግም ምጽአቱ ትንቢት ተናግረው አላቆሙም፡፡

ነቢዩ ዳዊት “እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም” በማለት ሲማጸን (መዝ.፻፵፫፥፯) ነቢዩ ኢሳይያስ ደግሞ “እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች፥ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” በማለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም እንደሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ (ኢሳ.፯፥፲፬) በዚህም የተስፋ ቃል “ኃይልህን አንሳ፤ እጅህንም ላክ” በማለት ነቢያት እየተማጸኑ ጾመዋል፡፡

የነቢያት ጾም (የገና ጾም) ከኅዳር ፲፭ ጀምሮ ለ ፵፫ ቀናት የሚጾም ሲሆን ፋሲካው (ፍቺው) በልደት በዓል ነው፤ ይህም ጾም በዘመነ ብሉይና በዘመነ ሐዲስ ቅዱሳንና ምእመናን ጾመውታል፡፡ እኛም አምላካችን ቸርነቱን እንዲያበዛልን፣ ከፈተና እንዲያወጣን፣ ወቅታዊውን ሀገራዊ ችግር ይፈታልን ዘንድ፣ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ እንዲሠውረን ጾሙን እንጹም!

የጌታችን ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና የቅዱሳን ነቢያት ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ አሜን!