ሥዕለ አድኅኖ

ክፍል አራት

ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ 

ታኅሣሥ ፳፯፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች እንዴት አላችሁልን!  እንኳን ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አደረሳችሁ! ልጆች ዘመናዊ ትምህርታችሁስ እንዴት ነው? የዓመቱ አጋማሽ እየደረሰ በመሆኑ በርትታችሁ በማጥናት ጥሩ ውጤት ማስመዝገብ እንዳለባችሁ በዚሁ አጋጣሚ ልናሳስባችሁ እንወዳለን! ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ ደግሞ በሰንበት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መማርን፣ ማገልገልን እንዳትረሱ፤መልካም!

ባለፈው  ስለ ሥዕለ አድኅኖ በተማርነው ትምህርት ሥዕለ አድኅኖ ሲሳሉ ምን ዓይነት ቀለማት መሆን እንዳለባቸውና የቀለማቱ ትርጒም (ምሳሌነት) ምን እንደሆነ በመጠኑ ተመልክተናል፡፡ በዚህ የትምህርት ክፍለ ጊዜ ደግሞ በሥዕለ አድኅኖ የተደረጉ ተአምራትን እንማራለን፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ስለ ሥዕለ አድኅኖ ባለፈው ትምህርታችን ስንማር ሥዕል ማለት ምን ማለት እንደሆነ አይተናል አይደል? ታስታውሳላችሁ ብለን እናስባለን! ቅዱሳት ሥዕላት ሲሳሉ የምንጠቀማቸው ቀለማት ምሥጢራቸው ምን እንደሆነም በመጠኑ ስንማር ነበር፡፡ በክፍል አራት ደግሞ በሥዕለ አድኅኖ (ቅዱሳት ሥዕላት) ከተደረጉ ተአምራት የተወሰኑትን ለአብነት እንመለከታለን፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ማርታ የምትባል መልካምና ደግ እንግዶችን በቤቷ የምታስተናግድ እመቤታችንን ከልቧ የምትወድ ሴት ነበረች፡፡ አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባል መነኩሴ ቤቷ በእንግድነት መጣ መስተንግዶ አድርጋለት ሊሄድ ሲል ወዴት እንደሚሄድ ጠየቀችው፡፡ ከዚያም መነኩሴው ቴዎድሮስ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚሄድ ነገራት፡፡ እርሷም ከኢየሩሳሌም አገር የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል እንዲያመጣላት ጠየቀችው፡፡ እርሱም “እሺ” ብሏት ሄደ፡፡

ልጆች ይገርማችኋል! አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሶ ሲመለስ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ምስለ ፍቁር ወልዳ (እመቤታችን ልጇ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ታቅፋ) ያለውን ሥዕል ገዛላትና ማርታ ወደምትኖርበት ጼዴንያ ወደሚባው አገር ሲጓዝ በሚያስፈራ ጫካ (ዱር) ውስጥ ወንበዴዎች አገኙት፤ ሊሸሽ (ሊሮጥ) ሲል ከሥዕሏ           ‹‹መንገድህን ሂድ›› የሚል ቃል ወጣ፤ ሳይፈራ ቀጥ ብሎ ወደፊት ተጓዘ (ሄደ) ማንም የተከተለውም ሆነ ሊጎዳው የፈለገ ማንም አልነበረም፡፡ እንደገናም አንበሳ መንገድ ላይ አገኘውና ሊበላው ሲጮህ ከሥዕሏ አስፈሪ ድምፅ ወጣና አንበሳውን አባረረው፤ የዚህን ጊዜ አባ ቴዎድሮስ በሥዕሏ የተደረገውን ተአምር ሲመለከት የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ለራሱ ሊያደርጋት ፈለገ፤ ‹‹ይህችን ተአምረኛ ሥዕል ወደ አገሬ እወስዳታለው ለማርታ አልሰጥም›› ብሎ በልቡ አሰበ ወደ ማርታ አገር ጸዴንያ መሄዱን ትቶ በሌላ መንገድ ለመሄድ ጉዞ ጀመረ፡፡

ልጆች! በሚገርም ሁኔታ ነፋስ ተነሣና የሚጓዝበትን መርከብ መንገዱን አቅጣጫውን አስቶ ወደ ጼዴንያ አገር ወሰደው፤ መሽቶም ስለነበር ወደ ማርታ ቤት ገብቶ አደረ፤ ማንነቱን ግን አልነገራትም፤ ሊነጋጋ ሲል ተነሣና ሊወጣ ሲል የመውጫው በር ጠፍቶበት ሲንከራተት ዋለ፤ ሲመሽ ገብቶ ተኛ አሁንም በሁለተኛው ቀን እንዲሁ አደረገ መሸበትና ገብቶ ተኛ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ሌሊት ተነሣና ማንም ሳያየው ሊወጣ ሲል በሩ ጠፋበት፤ ማርታ በየቀኑ ይህን የመነኩሴውን (አባ ቴዎድሮስን) ሁኔታ ትመለከት ነበር፤ ቀረብ ብላ ምን ሆነህ ነው? ሦስት ቀን ሙሉ ስትቅበዘበዝ ግራ ገብቶህ ከቦታ ቦታ ትመላለሳህ”  ብላ ጠየቀችው፤ አባ ቴዎድሮስም ሥዕል እንዲገዛላት የላከችው ሰው እንደሆነ እና ሥዕሏን ገዝቶ ሲመጣ የተደረገውን ተአምራት ሁሉ ነገራትና ይቅርታ ጠይቆ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ሰጣት፡፡ የተጠቀለለበትን መጎናጸፊያ ሲፈታ ከሥዕሊቷ (ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል) ወዝ ሲንጠፈጠፍ (ደስ የሚል መዓዛ ሲወጣ) ተመለከቱ፡፡ ማርታም በጣም ደስ አላት፤ በጸሎት ቤት አስቀመጠጫት፡፡ (መጽሐፈ ሐፈ ሐ   ስንክሳር መስረም ፲ ቀን የሚነበብ)

በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ከተደረጉ ተአምራት አንዱን ለአብነት ተመለከትን፤ ከዚህ ታሪክ በርካታ ትምህርት እናገኛለን፤ ለምሳሌ የእኛ ያልሆነውን ነገር መመኘት እንደማይገባ ከአባ ቴዎድሮስ እንማራለን፤ ምንም ቢያምረን ብንወደው የእኛ ያልሆነውን ነገር ለመውሰድ መመኘት አይገባም፤ ታማኞችና አደራን በአግባቡ የምንወጣ መሆን አለብን፡፡ ማርታ እመቤታችንን ከልቧ በመውደዷ እመቤታችን ድንቅ ነገር አደረገችላት፡፡

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ሌላው ደግሞ በቅዱስ ሚካኤል ሥዕል የተደረገውን ተአምር እንመልከት፤ አስተራኒቆስና አፎምያ የተባሉ ቅዱስ ሚካኤልን የሚወዱና በስሙ ዝክርን የሚዘክሩ ለችግረኞች (ለድሆች) የሚያባሉ የሚያጠጡ መልካም እና ደግ ክርስቲያኖች ነበሩ፤ አስተራኒቆስ ለሚስቱ ለአፎምያ “ምን ላድርግልሽ?” በማለት በጠየቃት ጊዜ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ዐሥሎ  እንዲያመጣላት ጠየቀችው፤ እርሱም ገዛላትና በጸሎት ቤቷ በክብር አስቀመጠችው፡፡

አስተራኒቆስም ታመመና ሞተ፤ አፎምያም በጾም በጸሎት ተወስና በእምነቷ ጸንታ፣ በመልካም ምግባር መኖር ጀመረች፡፡ በቅዱስ ሚካኤል ስምም ዝክር ትዘክርና ለችግረኞች ታበላ ነበር፤ በዚህ መልካም ምግባሯ ሰይጣን ቀናባትና ሊያሳስታት መጀመሪያ በሴት መነኮሳት ተመስሎ በመምጣት ጾም ጸሎት ማብዛት እንደሌለባት ነገራት፡፡ እርሷም ይህ ደግ ያልሆነ ምክር ነው፤ አልሰማችሁም አለቻቸው፡፡

በሌላ ቀን ደግሞ መልአክ መስሎ መጣና “እኔ ሚካኤል ነኝ” አላት፤ ቅድስት አፎምያም ስትመለከተው ምንም ነገር በእጁ አልያዘም፤ እርሷም “የእግዚአብሔር መልአክ ከሆንክ በእጅህ የመስቀል ምልክት ለምን አልያዝክም” አለችው፤ “ቤቴ ያለው የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ጋር አይመሳሰልም” ብላ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ይዛ ስትመጣበት ያ ሰይጣን ከአጠገቧ ብን ብሎ ጠፋ፡፡ በሌላ ቀን ሊጎዳት ሲመጣ ቅዱስ ሚካኤል ደረሰና አዳናት፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ሰኔ ፲፪ ቀን የሚነበብ)

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ሕገ እግዚአብሔር እየጠበቅን መጽሐፍ ያዘዘንን እየፈጸምን በመኖር በቅዱሳን ቃል ኪዳን ታምነን ስንጸልይ እግዚአብሔር ቅዱሳንን በመላክ ከክፉ መከራ   ይጠብቀናል፡፡ ቅድስት አፎምያ በቅዱስ ሚካኤል ቃል ኪዳን ስትታመን እንዳዳናት ከቅዱሳን መላእክት ሥዕላት ሥር ሆነን ስንማጸን በሥዕላቸው ድንቅ ተአምራት ይደረግልናል፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! በቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕል የተደረገውን ተአምርም እንመልከት፤ ዑልያኖስ የተባለ ሰው በነገሠበት ዘመን ቅዱስ ባስሊዮስ ሊቀ ጳጳስ ነበረ፤ ይህ ንጉሥ የማይገባ ነገር ይሠራ ጀመር፤ ምእመናንን ሃይማኖታቸውን እንዲክዱ መከራ ሲያደርስባቸው ባገኘው ጊዜ መክሮ ከስሕተቱ ሊመልሰው ሲመጣ ቅዱስ ባስልዮስን አሠረውና ከምሄድበት ስለስ እገድልሃለው በማት ዝቶበት( አስፈራርቶት) ሄደ፡

በእሥር ቤት ውስጥም ቅዱስ መርቆሬዎስ በፈረስ ተቀምጦ በእጁ ጦር ይዞ የተሳለ ሥዕል ነበረ፤ ቅዱስ ባስልዮስ በሥዕሉ ፊት ሆኖ ሲጸልይ ሥዕሉ ከቦታው ለተወሰነ ጊዜ ተሠወረ      (ታጣ)፡፡  ንጉሥ ዑልያኖስንም ገድሎት ትንሽ ቆይቶ ወደ ቦታው ተመለሰ፤ ቅዱስ ባስልዮስም ሥዕሉን ሲመለከት ጦሩ ላይ ደም ሲንጠባጠብ ተመለከተ፤ ከዚያም ‹‹ ዑልያኖስን ገደልከውን?›› አለው፤ የቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕልም ራሱን ዘንበል አደረገ፤ (አዎ እንደ ማለት ዘንበል ብሎ መለሰለት) ቅዱስ ባስልዮስም እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ኅዳር ፳፭ የሚነበብ)

ልጆች! በሥዕለ አድኅኖ ብዙ ተአምራት ተደርገዋል፤ አሁንም ይደረጋሉ ፤እኛ በእምነት ሆነን በቅዱሳን ሥዕላት ፊት ሆነን ስንጸልይ ቅዱሳን በሥዕላቸው ድንቅ ተአምራትን ያደርጋሉ፡፡

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች!  በሥዕለ አድኅኖ ብዙ ተአምራት ተደርገዋል፤ ወደፊትም እንደ እምነታችን ጽናትና መንፈሳዊ ሕይወታችን ብስለት በሥዕለ አድኅኖ ድንቅ ተአምራትን ልንመለከት እንችላለን፡፡ ለዛሬ ይቆየን፤ በሚቀጥለው ሥዕለ አድኅኖ (ቅዱሳት ስዕላትን) እንዴት አክብረን መያዝ እንዳለብን እንማራለን፡፡

ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ በዘመናዊ ትምህርታችሁ በርትታችሁ ተማሩ፤ ለወላጆቻችሁ መታዘዝን፣ ለሰዎች መልካም ማድረግን እንዳትረሱ፤ በሰንበት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መንፈሳዊ ትምህርትንም ተማሩ፡፡ ቸር ይግጠመን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

የሃይማኖት ተክል!

ታኅሣሥ ፳፫፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ድንቅ በሆነው የፈጣሪ ሥራ ሰው ሆነን ተፈጥረን በዚህ ዓለም ላይ ስንኖር የሕይወታችን መሠረት በሆነው ሃይማኖት ጸንተንና በቀናው መንገድ ተጉዘን የመንፈስ ፍሬን ለማፍራት እንዲቻለን ነው፡፡ የማንኛውም መንፈሳዊነት መሠረት ሃይማኖት ነውና፡፡ አንድ አምላክን ማመን ለእርሱ መታመን ሃይማኖት ነውና፤ ይህ ምሥጢር ገብቷቸው፣ በድንቅ ሥራቸው አብርተው፣ ፍጹም ተጋድሎአቸውን ጨርሰው ለአምላካቸው እውነተኛ ምስክሮች በመሆን ርስተ መንግሥተ ሰማያትን የወረሱ ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን የቤተ ክርስቲያናችን ዕንቁ ፈርጥ በመሆናቸው እናከብራቸዋለን፡፡

“የሃይማኖት ተክል” የተባለው ቅዱስ አባታችን ኢትዮጵያዊው ሐዋርያ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የከበረች ልደት በዓሉ በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ይከበራል፡፡ ጻድቁ በብሥራተ ቅዱስ ሚካኤል መሠረትም በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ልዩ ስሙ ኢቲሳ በሚባል ቦታ መጋቢት ፳፬ ተፀንሰው ታኅሣሥ ፳፬ የተወለዱት ከአባታቸው ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው እግዚ ኅረያ ነው፡፡

በተለወዱ በሦስተኛው ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ     ወርደው    ‹‹ሐዱ  አብ  ቅዱስ፤   አሐዱ  ወልድ  ቅዱስ፤  አሐዱ  ውእቱ  መንፈስ  ቅዱስ፤  አንዱ  አብ  ቅዱስ  ነው፤  አንዱ  ወልድ  ቅዱስ  ነው፤  አንዱ  መንፈስ  ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት አጋእዝተ ዓለም ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ ወላጆቻቸው ያወጡላቸው ስም ‹‹ፍሥሐ ጽዮን››  የሚል ቢሆንም‹‹ተክለሃይማኖት›› ደግሞ ጌታችን እራሱ ነው፡፡

የሃይማኖት ተክል የተባሉት ቅዱስ አባታችን የወንጌልን ቀንበርን ተሸክመው፣ ሀገራችን ኢትየጵያን በዕርፈ መስቀል ያረሱ፣ ቅዱስ ቃሉን ሰብከውና አስተምረው፣ እውነተኛ ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ሃይማኖትን ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን ለዓለም አሳውቀው፣ ጣዖታትን ሰባብረው ቀጥቅጠው ያጠፉ፣ ብዙዎችን ከኃጢአት ጎዳና መልሰው ለርስተ መንግሥተ ሰማያት ያበቁ ታላቅ አባት ናቸው፡፡

የአባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ጸሎት፣ አማላጅነትና ረድኤት አይለየን፤ አሜን!!!

ምንጭ፡ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት

 

‹‹እኔ ሰላማዊ ነኝ!›› (መዝ.፻፲፱፥፯)

ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ 

ታኅሣሥ ፳፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ሰላም  “ፍጹም ጤና፣ ዕረፍት፣ ዕርቅ፣ ፍቅር፣ አንድነት” ነው፡፡ (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ገጽ ፰፻፷፮) አንድ ሰው ሰላም አለው ሲባል ጤነኛ እና ለሰዎች ፍቅር ያለው ኅብረትን አንድነትን የሚወድ ማለት ነው፡፡ ሰላም ለሰዎች ሁሉ አስፈላጊና መሠረታዊ ከሆኑ ነገሮችም አንዱ ነው፤ ማንኛውንም ነገር ለማከናወን ቅድሚያ ሰላም መሆን አስፈላጊ ነው፤ በሕይወታችን ደስተኛ ሆነን ለመኖር፣ አእምሮአችንን ከጭንቀት ነጻ ለማድረግ፣ ለሰዎች መልካም ነገርን ለማሰብ እኛም ደስተኛ እና ጤነኛ ለመሆን ሰላማዊ መሆን አለብን፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ምእመናን በላከው መልእክቱ እንዲህ ይመክረናል፤ ‹‹…ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ…፡፡›› (ሮሜ ፲፪፥፲፰) ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር እኛ የሰላም ሰዎች ነገሮችን በትዕግሥት የምናልፍ፣ ለሰዎች መልካም የምናስብ ልንሆን ይገባል፡፡

ውድ ክርስቲያኖች! የሰላም መገኛው የት ነው?! ለመግቢያ ያህል ሰላም ስለሚለው ኃይለ ቃል ገለጽን እንጂ ርእሰ ጉዳዩን የመረጥነው ስለ ሰላም ምንነት በስፋት ለማብራራት አይደለም፤ ሰላማዊ ሰው ስለመሆን  እንጂ! በርእሳችን ላይ ‹‹እንዘ ሰላማዊ አነ፤ እኔ ሰላማዊ ነኝ›› የሚለውን ኃይለ ቃል የተናረው ልብ አምላክ ንጉሥ ዳዊት ነው፤ መተርጉማን አበው ነቢዩ ንጉሥ ዳዊት ይህንን ደስ የሚል ከመንፈስ ፍሬዎች መካከል አንዱ የሆነውን ቃል፤  ‹‹የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፣ ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት›› (ገላ.፭፥፳፪) መናገሩ ለምን እንደሆነ ሲያመሠጥሩ ከሕይወት ታሪኩ ክፍል አንዱን ይተርካሉ፤ ነገሩ እንዲህ ነው!

ንጉሥ ዳዊት በነቢዩ ሳሙኤል አማካኝነት ተቀብቶ ከነገሠ በኋላ ጎልያድን በመግደሉ በሕዝቡ ዘንድ ባገኘው ከበሬታ ምክንያት ንጉሥ ሳኦል ሊገድለው ተነሣ፤ ብላቴናው ነቢይ ዳዊትም ከሳኦል ፊት ሸሽቶ ሄደ፤ በቀርሜሎስም ከባለሟሎቹ ጋር ተቀመጠ፡፡ በዚያም ናባል የሚባል ሰው ነበር፤ ሚስቱም አቢግያ ትባላለች ዳዊት በዚያ ስፈራ በመኖሩ የአካባቢውን ሰዎች ንብረት በሽፍቶች (በቀማኞች) እንዳይወሰድ ከለላም ሆነ፤ ዳዊትም የሚገባውን ግብር እንዲያገባ ለናባል መልእክተኞችን ላከ፤ ናባል ግን ከስጦታው ይልቅ ስድብንም ጨምሮ የእንቢታን ምላሽ ሰጠ፡፡ ንጉሥ ዳዊት በዚህ ተቆጥቶ ናባልና የእርሱ የሆኑትን ሁሉ ያጠፋ ዘንድ ወሰነ፤ ይህንን ነገር የናባል ሚስት አቢግያ ሰማች፤ ከዚያም የሚገባውን እጅ መንሻ ይዛ ወደ ንጉሥ ዳዊት ገሰገሰች፤ ከእግሩም ሥር በግንባሯ ተደፍታ እጅ ነሣች፤ ሊወስድ  የመጣውን ርምጃ (ቅጣት) እንዳይፈጽም እንዲህ አለችው ‹‹…ወደ ደም እንዳትገባ አጅህም ራስህን እንዳታድን የከለከለህ እግዚአብሔር ነው …›› (፩ኛ ሳሙ. ፳፭፥፳፮) እጅ መንሻውንም ሰጠች፤ ንጉሥ ዳዊትም የሰላም ሰው ነውና የአቢግያን የሰላም መልእክት ተቀብሎ ከጸብ ይልቅ ሰላምን፣ ከበቅል ይልቅ ይቅርታን መረጠ እንዲህም ሲል አመሰገነና ‹‹…ዛሬ እኔን ለመገናኘት አንቺን የሰደደ የእስራኤል አምላክ  እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ ወደ ደም እንዳልሄድ በእጄም በቀል እንዳላደርግ ዛሬ የከለከለኝ አእምሮሽ የተመሰገነ ይሁን  አንቺም የተመሰገንሽ ሁኚ…›› አላት፡፡ (፩ኛ ሳሙ. ፳፭፥፳፮) የሰላም ሰው ንጉሥ ዳዊት ስለ መልካምነቱ፣ ስለ ይቅርታው በትዕቢት የተገዳደረው ናባል ግን ተቀሥፎ ሞተ፡፡

ውድ ክርስቲያኖች! የሰላም መገኛው የት ነው ?!  ነቢየ እግዚአብሔር ንጉሥ ዳዊት ለተበደለ ሊፈርድ የበደለን ሊቀጣ በእግዚአብሔር የተመረጠ የሕዝቡ መሪ ሆኖ ሳለ በትዕቢት የተገዳደረው ናባል ያስቆጣውን ልቡን ብልህና አስተዋይዋ አቢግያ በሰላማዊ ንግግሯ አበረደችው፡፡ ንጉሠ ዳዊት ሰላሙን ከይቅርታው አገኘው፤ የበቀል ጉዞውን በትዕግሥት ገታው፤ በአንድ ሰው ምክንያት ጉዳዩ የማይመለከታቸውን ከመቅጣት (ከማጥፋትና) ደስታውን ከሚነጥቅ፣ ዕረፍቱን ከሚነሣ፣ ፍቅርን ከሚያሳጣ፣ ጤናውን ከሚያቃውስ፣ ከጸጸት አዘቅት ከሚከት ከሰላም እጦት ራሱን ጠበቀ፡፡

ውድ ክርስቲያኖች! የሰላም መገኛው የት ነው?!  ሰላምን ፍለጋ ዘምረናል፤ ጸልየናል፤ እኛ ሰላማዊ ለመሆን ምን ያህል ጥረናል! “ሰላም አውለን” ብለን ከቤት ስንወጣ ሰላማዊ ለመሆን፣ ጥላቻን በፍቅር፣ በደልን በይቅርታ ለመለወጥ ምን ያህል ጥረናል?! ጤናችንን የሚያቃውስ፣ ፍቅራችንን የሚያደፈርስ፣ አንድነታችንን የሚበታትን ጥላቻን፤ ከልባችን አንግሠን፣ ሰላማችንን የሚያርቅ ሰብእናችንን የሚያጎድፍ፣ ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለየንን ቂም አርግዘን ሰላምን እንዴት ማግኘት ይቻላል?! አምላካችን ጥላቻን በፍቅር፣ በደልን በይቅርታ ቀይሮ ሰላማችንን ሰጠን፤ ‹‹..ሰላምን እተውላችኋለሁ፤ ሰላምን እሰጣችኋላሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጣችሁ አይደለም…›› እንዲል፡፡ (ዮሐ.፲፬፥፳፯)፤ ፈለጉን እንከተል እንመስለውም ዘንድ ‹‹ከእኔ ተማሩ፤ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና›› ብሎ ነገረን፤ በምግባራቸው ሊመስሉት የተከተሉት፣ መጠራታቸውን በመመረጥ መመረጣውን በመጽደቅ ያጸኑ ቅዱሳን አባቶቻችን የሰላምን ጥቅም በጥልቀት ተረድተው እኛም እንጠቀምበት ዘንድ እንዲህ ይመክሩናል!፤ ‹‹…በሰው ሁሉ ፊት መልካም የሆነውን አስቡ ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ …፡፡›› (ሮሜ ፲፪፥፲፰)

ውድ ክርስቲያኖች! የሰላም መገኛው የት ነው ?! ሰላም ከራሳችን ይጀምራል፡፡ እያንዳንዳችን ሰላማዊ ከሆንን ሰላማዊ ቤተሰብ ይኖረናል፤ ሰላማችን ከእኛም አልፎ ለጎረቤት፣ ከፍ ሲል ለከተማ ከዚያም ለአገርና ለዓለም ይተርፋል፤ ሰላም ከየትም አይገኝም፤ የሰላም መፍለቂያዋ ከቂም በቀል ከራቀ፣ ከጥላቻ ከጸዳ፣ ፍቅርን ካነገሠ፣ አንድነትን ከመረጠ ልባችን ነው፤ ለዚህም ነው፡፡  ጠቢቡ ሰሎሞን በምሳሌው ‹‹…አጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፤ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና…›› በማለት የሚመክረን የሰላም መገኘዋ፣ የሕይወት መውጫ ከሆነ ልባችን ነውና፡፡ (ምሳ. ፬፥፳፫)

‹‹ሕይወትን ሊወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚፈልግ ሰው ምላሱን ከክፉ፣ ከንፈሮቹንም ተንኮልን ከመናገር ይከልክል፤ ከክፉ ፈቀቅ ይበል፤ መልካምንም ያድርግ፤ ሰላምን ይሻ ይከተላትም…፡፡›› (፩ኛ ጴጥ.፫፥፲፩፤መዝ.፴፫፥፲፬)

ውድ ክርስቲያኖች! የሰላም መገኛው የት ነው ?! ሰላምን ከፈለግናት ከራስ ወዳድነት እንለይ፤ ምክንያቱም ‹‹የዓለማችን ችግር ሁል ጊዜ ምንጩ ራስ ወዳድነት ነውና›› በአንድ ወቅት እንዲህ ሆነ፤ ሁለት መነኮሳት ስለ ሰላም መደፍረስ፣ ስለጸብ መነሻ ምን እንደሆነ መጠያየቅ ጀመሩ፤ አንደኛው እንዲህ ሲል ጠየቀ! ‹‹ሰዎች ሰላማቸውን የሚያጡት፣ ፍቅራቸው የሚደፈርሰው በምን ምክንያት ነው?››! አንደኛው በምሳሌ ያስረዳው ዘንድ የያዘውን ዳዊት (የጸሎት) መጽሐፍ ተቀበለውና እንዲህ ያስረዳው ጀመር፤ ‹‹ይህ ዳዊት (የጸሎት መጽሐፍ) ያንተ ነው፤ እኔ ግን እነጥቅህና የእኔ ነው እልሃለው፤ አንተ ደግሞ የእኔ ነው ትላለህ፤ የዚህን ጊዜ በመካከላችን ጸብ ይጀመራል፤ ፍቅራችን ይጎረብጣል፤ ሰላማችን ይናጋል›› በማለት አስረዳው፤ በምሳሌም በተግባር ለማሳየት ብሎ የጓደኛውን ዳዊት (የጸሎት) መጽሐፍ ነጠቀውና  ‹‹የእኔ ነው›› አለው፤ ያም የዋህ መነኩሴ ‹‹አይ የእኔ ነው፤ የአንተ አይደለም›› ማለት ሲገባው እርሱ ግን ‹‹እሺ የአንተ ነው፤ ውሰደው›› ብሎ የእራሱን የሆነ ዳዊት (የጸሎት መጽሐፍ) ተወለት! በመነኮሳት (በአባቶች) ዘንድ ፍቅር እንጂ ጸብ የለምና፤ የእኛ እንጂ የእኔ የሚባል ነገር የለምና! ሰላምን ከሌላ ሰው ከሩቅ ሳይሆን ከራሳቸን እንፈልጋት፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

አማናዊ ብርሃን

ታኅሣሥ ፲፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

እውነተኛው ብርሃን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎችን ከገቡበት የኃጢአት ባርነትና የጨለማ ዓለም ለማውጣት ወደዚህች ምድር እንደመጣ፣ መከራን ተቀብሎ፣ በመስቀል ተስቅሎ፣ ሞቶ፣ ተነሥቶ ነጻ እንዳወጣን ቅዱሳኑ ነቢያት ሰብከዋል፡፡ ምሥጢረ ሥጋዌውን ነገረ ድኅነትን በሚገባ አስተምረዋል፡፡

ከድንቁርና ወደ ፍጹም ዕውቀት ያደረሰን፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ያወጣን፣ ከሞት ወደ ሕይወት ያሸጋገረን ጌታ እርሱ ዓለም ብርሃን ነው፡፡ “አነ ውእቱ ብርሃኑ ለዓለም” እንዲል፡፡ (ዮሐ.፰፥፲፪) ነቢያትም ጌታን በብርሃን እየመሰሉ ሥጋዌውን ተናግረዋል፡፡ ነቢዩ ዳዊትም እንዲህ አለ፤ “ብርሃን ለጻድቃን፥ ደስታም ለልበ ቅኖች ወጣ።” (መዝ.፺፯፥፲፩) በመጽሐፈ ኢሳይያስም ደግሞ “ለአሕዛብ ብርሃን አድርጌ ሰጥቼሃለሁ” ተብሎ ተጽፏል፡፡ (ኢሳይያስ ፵፱፥፮)

መጽሐፈ መዝገበ ታሪክ የጌታን ብርሃንነት እንዲህ አስፍሮታል፡፡ “ብርሃንም ቢባል እንደ ፀሐይ እንደ ጨረቃ ብርሃን ጠፈር ደፈር የሚከልክለው መዓልትና ሌሊት የሚፈራርቀው አይደለም፡፡ የማይጠፋ የማይለወጥ አማናዊ ብርሃን ነው እንጂ፤” (ገጽ ፻፮) ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደገለጸው “እግዚአብሔር ብርሃን ነው፤ ጨለማም በእርሱ ዘንድ ከቶ የለም የምትል ይህች ናት።” (፩ኛ ዮሐ. ፩፥፭) ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ይህን ለመዘከር ከታኅሣሥ ፲፬ እስከ ፳ ድረስ ያለውን ወቅት “ብርሃን” ብላ ሰይማዋለች፡፡

ብርሃን የሆነው አምላካችንና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኃጢአት ማዕበል እየተናወጠች፣ በችግር መከራ ተጨንቃ፣ በነፋሱ ውዥንብር ከግራ ቀኝ እየተማታች፣ በምድር መናወጥ እየተንቀጠቀች፣ በጎርፍ እየሰጠመች፣ በእሳት ውእያት እየተለበለበች ወደ ድቅድቅ ጨለማ ከተለወጠችው ዓለም ያውጣን፤ አሜን!!!

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

ተስፋ መቁረጥ የኅሊና ሞት!

                                                                                                                                                                  ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ 

ታኅሣሥ ፲፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ኅሊና የሚለውን ቃል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ “የአፍአ፣ የውስጥ ሕዋስ፣ ረቂቅ፣ ውሳጣዊ፣ ተነሣሽ፣ ተንቀሣቃሽ” በማለት ይገልጡታል፤ (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ገጽ ፬፻፸፯)

ኅሊና ጥሩና በጎውን፣ ትክክልና ስሕተቱን የሚለይ የአእምሮ ክፍል ነው፤ የራስ መመዘኛ፣ ክፉና በጎውን መለያ፣ የግላዊ ሂስ ማቀነባበሪያ፣ የነፍስ ክፍል በማለትም ይተነትኑታል፡፡ ኅሊና በጎውንና ክፉውን የምንለይበት መልካም ስንሠራ ሰላም፣ መረጋጋት እንዲሰማን፣ ስንበድልና ሕግ ስንተላለፍ ወቀሳን የሚያደርስብን ነው ፤ ‹‹..እነርሱም ይህንን ሲሰሙ ኅሊናቸው ወቀሳቸውና ከሽማግሌዎች ጀምሮ  እስከ ኋለኛዎቹ አንድ አንድ እያሉ ወጡ ….›› (ዮሐ.፰፥፱) አበው ኅሊናን  ‹‹እግዚአብሔር በሰው ልጅ ውስጥ ያስቀመጠው እውነተኛ ዳኛ ነው›› በማለትም ይገልጡታል፡፡ ዛሬ በዚህ መልእክታችን ማስገንዘብ የፈለግነው ስለ ኅሊና ምንነት በጥልቀት መመልከት ሳይሆን ተስፋ መቁረጥ ስለሚያመጣብን የኅሊና ሞት ነው፡፡

ተስፋ ለክርስቲያኖች ሕያው ነው፤ ግዑዝ አይደለም ወይም ቁስ አይደለም ሕይወት ያለው ነው እንጂ፤ ‹‹…በእግዚአብሔር ክብርም ተስፋ እንመካለን፤ ይህም ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ፣ ትዕግሥትም ፈተናን፣ ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን በመከራችን ደግሞ እንመካለን፤ በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለ ፈሰሰ ተስፋ አያሳፍረንም›› (ሮሜ ፭፥፲፭) ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጠው፤ ተስፋ የእምነታችን ምንጭ ነው፤ የተስፋ ምንጭ ወይም መገኛው ደግሞ የሁሉ ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው፤ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ምእመናን በላከው መልእከቱ ‹‹…የተስፋ አምላክም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በተስፋ እንድትበዙ በማመናችሁ ደስታንና ሰላምን ሁሉ ይሙላባችሁ…›› (ሮሜ ፲፭፥፲፫) በማለት ገልጾልናል፡፡

ሰው ምግብ ሳይመገብ፣ ውኃም ሳይጠጣ ለተወሰነ ጊዜ መቆየት ይችላል፤ አየርም አጥሮት እንዲሁ ለደቂቃዎችም  ቢሆን በሕይወት የመኖር ዕድል አለው፤  ተስፋ ከቆረጠ ግን ለሰከንድ መኖር አይችልም፡፡ በዚህ ምድር ላይ እየተቸገርን፣ በፈተና ወጀብ ታጅበንም፣ እየተሰደድንም እየኖርን ያለነው ነገን ከዛሬ የተሻለ ሆኖ እናገኘዋለን በሚል ተስፋ ነው፤ ተስፋ ባይኖረን  ከትናንት አልፈን ዛሬን ባላየናት፣ ዛሬ ላይ ቆመን ነገን ባልናፈቅናት ነበር፡፡

ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ በላከለት አባታዊ ምክሩ የኅሊናን መሞት ምን ያህል ለጥፋት እንደሚዳርግ እንዲህ ይገልጠዋል፤ ‹‹…እምነትና በጎ ኅሊና ይኑርህ፤  አንዳንዶች ኅሊናን ጥለው መርከብ ያለ መሪ እንደሚጠፋ በእምነት ነገር ጠፍተዋልና›› (፩ኛ ጢሞ.፩፥፲፱) መርከብ ያለመሪ በባሕር ላይ ቢጓዝ ዕጣ ፈንታው ከጥልቁ ሰጥሞ መጥፋት ነው፡፡

ሰዎች በተስፋ ከመቁረጥ የተነሣ ኅሊናቸውን ሲጥሉ፣ ማገናዘብ ሲያቁሞ፣ ሰብእናቸውን አጥተው፣ ከሕገ እግዚአብሔርም ወጠተው እንደሚጠፋ እንስሳት ሆነው በራሳቸው ላይ በሚወስዱት ያልተገባ እርምጃ፣ በምድር ኑሮአቸው ጨልሞ፣ ከሞት በኋላ ባለው ሕይወታቸውም ዕጣ ፈንታቸው ከዲያብሎስና ሠራዊቱ ጋር እሳቱ ከማይጠፋ ትሉ ከማያቀላፋ ዘለዓለማዊ እሳት ይሆናል፡፡ የዚህ ሁሉ ምክንያቱ በእምነት ነገር መጥፋት ነው፡፡ እምነት ከሌለ ተስፋ አይኖረውም፤ ተስፋ ከሌለው፣ በጎ ኅሊና አይኖረውም፤ ከጽድቅ ሳይሆን ከበደል፣ ከሕይወት ሳይሆን ከሞት ያደርሳል፡፡

ከጨለማው ባሻገር ብርሃን፣ ከአቀበቱ ጀርባ ለምለም ሜዳ፣ ከኀዘን ባሻገር ደስታ፣ ከወጀብና ከአውሎ ነፋስ በኋላ ጸጥታና መረጋጋት፣ ከትንሣኤ በኋላ ሕይወት እንዳለ የሚያምን ክርስቲያን፣ የሚገጥመውን ፈተና፣ መከራና ስደት፣ ማጣት፣ መገፋትን በአኮቴት ተቀብሎ፣ ነገን እያለመ በትዕግሥት ይጠብቃል፤ ምክንያቱም እግዚአብሔርን አምነው የሚያደርጓት ተሰፋ እንደማይጨበጥ ደመና (ጉም) አልያም ርቆ እንደተሰቀለ ዳቦ ሳይሆን፣ የሚፈጸም፣ እውነት የሆነ ነው፡፡ በእርሱ ዘንድ ያለን ተስፋ ምኞትና ናፍቆት ብቻ ሳይሆን አለኝታና መተማመን የሚገኝበት ነውና። ነቢዩ ዕንባቆም በመከራ ጊዜ እንኳን ቢሆን ጸንቶ መገኘት እንደሚገባ እንዲህ በማለት የገለጸው ለዚህም ነው፤ ‹‹….ምንም እንኳ በለስም ባታፈራ፣ በወይንም ሐረግ ፍሬ ባይገኝ፣ የወይራ ሥር ቢጎድል፣ እርሾችም መብልን ባይሰጡ፣ በጎችም ከበረት ቢጠፉ፣ ላሞችም በጋጣ ውስጥ ባይገኙ እኔ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይለኛል፤ በመድኃኒቴ አምላክ ሐሤት አደርጋለው፡፡››  (ዕን.፫፥፲፯)

በእግዚአብሔር ላይ እምነታቸው የጸና፣ ተስፋቸው የለመለሙ፣ ኅሊናቸው ሳይሞትባቸው የፈለጉትን አግኝተዋል፤ ከገቡበት ስምጥ፣ ከሰጠሙበት አዘቅት፣ ወጥተዋል፤ ከከበባቸው ጨለማ፣ ከወረደባቸው የመከራ ዶፍ፣ በመንገዳቸው የገጠማቸው ጉድባ ተሻግረዋል፤ በጉዟቸው የተጋረጠውን ወጀብ ተስፋን ይዘው፣ ከኅሊና ሞት አምልጠው ካሰቡበት ደርሰዋል፤ የሻቱትን አግኝተዋል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ብሎ እንደተጻፈ፤ ‹‹የሁሉ ዐይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፤ አንተም ምግባቸውን ትሰጣቸዋለህ››  (መዝ.፻፵፬፥፲፭)‹‹…በሁሉ እንገፋለን እንጂ አንጨነቅም፤ እናመነታለን እንጂ ተስፋ አንቆርጥም…፡፡›› (፪ኛ ቆሮ.፬፥፰)

እስራኤላውያን በግብጽ ከነበሩበት የሰቆቃ፣ የባርነት ሕይወት እግዚአብሔር በሊቀ ነቢያት መሪነት አውጥቷቸው ወደ ተስፋይቱ አገር ከነዓን ይጓዙ በነበረበጽት ጊዜ በኤርትራ ባሕር በፊሀሒሮት በሚባል ሥፍራ በነበሩበት ጊዜ ልበ ደንዳናው ፈርዖን፣ ማርኮ ዳግመኛ በባርነት ሕዝቡን ለመገዛት በማሰብ ሠራዊቱን አስከትሎ መጣ፤ እስራኤላውያን ከፊታቸው የኤርትራ ባሕር ተጋረጠ፤ ከኋላቸው የፈርዖን ሠራዊት ተከተለ፤ እምነታቸው ላልቶ በግብጻውያን ያደረገውን ድንቅ ሥራውን ረስተው ተስፋ ቆረጡ፤ ‹‹…በበረሃ ከምንሞት ብንገዛላቸው ይሻላል…››  እስከማለት ደረሱ፤ ሊቀ ነቢያት ሙሴ እምነቱ የጸና፣ በእግዚአብሔር ያለው ተስፋው የታመነ ነበርና አንደበቱን ሞልቶ ሕዝቡን እንዲህ አላቸው፤ ‹‹…አትፍሩ! ዛሬ የምታዩአቸውን ግብጻውያን ለዘለዓለም አታይዋቸውምና ቁሙ፤ ዛሬ ለእናንተ የሚያደርገውን እግዚአብሔርን ማዳን እዩ፡፡›› (ዘጸ.፲፬፥፲፫)

ሊቃውንት ሲያስተምሩ በእግዚአብሔር ለታመነው ለሊቀ ነቢያት ሙሴ በኤርትራ ባሕር መሐል የመጓዢያ ለምለም መስክ በእምነት መነጽር ይታየው ነበር፤ በእግዚአብሔር የሚታመን በድቅድቅ ጨለማ መሐል ብርሃን፣ ከከበቡት ተራሮች ባሻገር ለምለም መስክ ይታየዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ዘመነ ሰማዕታት ተብሎ በሚታወቀው የመከራ ዘመን ክርስቲያኖች አምልኮታቸውን በነጻነት መፈጸም፣ በዓላቸውን በደስታ በአደባባይ ማክበር ባልቻሉበት የጭንቅ ወቅት ተስፋ ሳይቆርጡ በግበበ ምድር (በካታኮም) መልእክታትን በኮድ  (በምሥጢር) በመጻፍ  በሰው ሰውኛ አይቻልም የተባለውን የመከራ ዘመን አልፈው፤ ለተከታይ ትውልድ ደማቸው ዘር፣ አጽማቸው አጥር (ከለላ)፣ ሆኖ ጠፉ ሲባል እየበዙ፣ ሞቱ ሲባል እየተኩ ክርስትናን አስቀጥለዋል፡፡

ክርስትና በደስታ ጊዜ የሚያምኑት ብቻ ሳይሆን በመከራ ጊዜ በሕይወት የሚገልጡት ነው፤ ታዲያ ይህን ለማድረግ ከኅሊና ሞት መጠበቅ ያሻል፤ ከኅሊና ሞት ለመዳን ደግሞ እምነት፣ ተስፋና ፍቅርን መያዝ ግድ ይላል፡፡

በአንድ ወቅት እንዲህ ሆነ፤ የሶርያው ንጉሥ ወልደ አዴር ሠራዊቱን ሰብስቦ ሰማርያን ከበባት፤ የሚገባም የሚወጣም ጠፋ፤ በሰማርያ ታላቅ ረኃብ ሆነ፤  ሰው የሚበላው ጠፍቶ የርግብ ኩስ  እስኪመገቡ ደረሱ፤ ከዚያም  የከፋ ነገርን አደረጉ! እግዚአብሔር ሕዝቡን ይታደግ ዘንድ በነቢዩ ኤልሳዕ አማካኝነት ረኀባቸው እንደሚወገድ መልእክት ለንጉሡ ተነገረው፤ ንጉሡ ኢዮራም ግን ከነበረው ረኃብ ጽናት የተነሣ ተስፋ ቆርጦ ነበርና ‹‹እግዚአብሔር በሰማይ መስኮቶች ቢያደርግ ይህ ነገር ይሆናልን..›› በማለት የተስፋ መቁረጥ እምነት መጉደል ያለበትን ንግግር ተናገር! (፪ኛ ነገ.፮፥፳፭)

ነቢዩ ኤልሳዕም ‹‹…እነሆ በዓይኖችህ ታየዋለህ፤ ከዚያም አትቀምስም አለ…›› (፪ኛ ነገሥ. ፯፥፩-፮) ነቢዩ ኤልሳዕ እንደተናገረው ሆነ እግዚአብሔር ይችላል፤ በአራት ለምጻሞች አማካኝነት ሶርያውያንን አስደንብሮ ከከተማው በራፍ እንዲሸሽ አደረገ፤ ሕዝቡም ያጣውን መብል (እህል) ከከበቧቸው ጠላቶቻቸው ሰፈር አግንቶ ተመገቡ፡፡ ሶርያውያን የጦር ሰፈራቸውን ለቀው መሄዳቸውን የሰማው ንጉሥ ሊመለከት ሲወጣ ሕዝቡ ገፍትሮ ጣለው፤ ረግጠውትም ሞተ፤ የእግዚአብሔር ነቢይ ኤልሳዕ ‹‹…እነሆ በዓይኖችህ ታየዋለህ፤ ከዚያም አትቀምስም …›› ብሎ እንደተናገረው እግዚአብሔር ለሕዝቡ ምግብን ሰጠ፤ ተመገቡም፤ ንጉሡም ተመለከተ፤ ግን አልተመገበውም፤  ምክንያም አስቀድሞ በኅሊናው ሞቷልና፡፡

አንዳንድ ጊዜ ነገሮች ሁሉ ሲቆላለፉ ሊሆን የሚችለው የማይሆን መስሎ ይታየንና ከማስተዋል ማነስና፣ ከእምነት መጉደል የተነሣ እንዴት ይሆናል? በሚል ሥጋዌ አመለካከትና እሳቤ የተስፋ መቁረጥ ንግግር ከአንደበታችን ይደመጣል፤ የኅሊናን ሞት ቀድመን እንሞታለን፤ እግዚአብሔር ግን ይችላል፡፡ የእኛ ኃላፊነት በማንኛውም ነገር በምንችለው መጠን ያቅማችንን ማድረግ ከዚያም እንደ ካህኑ ዔሊ ‹‹…እርሱ እግዚአብሔር ነው፤ ደስ ያሰኘውን ያድርግ…›› ልንል ይገባል፡፡ (፩ኛ ሳሙ.፫፥፲፰) እግዚአብሔር በአራት ለምጻሞች፣ ሰዎች በናቋቸው፣ ከማኅበረሰቡ በተገለሉ ሰዎች አማካኝነት ጠላቶቻቸውን አሳዶ የሕዝቡን ታሪክ ለወጠው፤ በእግዚአብሔር ከታመንን ሁሉን ማድረግ ስለሚቻል በአንዳች ነገር ተስፋን አንቆርጥም፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

የፍቅር ምርኮዎች

ታኅሣሥ ፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ፍጹም በሆነ ልዩ የልብ ስሜትና ኃይል ከራስ በላይ ለሌላ የሚኖር ደስ የሚያሰኝ መንፈስ፣ በሥቃይ ውስጥ የሚገኝ፣ እጅግ አስደናቂ ተፈጥሮ “ፍቅር ነው!” ፍቅር ሁለመናውን ይሰጣል፤ እንደራሱ ይወዳል፤ ለወደደው ያስባል፤ ይንገላታል፤ ይሠቃያል፤ ይሞታል፡፡

የፍቅር ባለቤት ጌታ ነው፤ በፍጹም ፍቅሩ ለሰው ልጆች ባሕይሪውን ዝቅ ያደረገ፣ ፈጣሪ ሆኖ ሳለ በሰዎች መካከል የተመላለሰ፣ እንደ ወንጀለኛ ተቆጥሮ በፍርድ ሸንጎ የቀረበ፣ የተከሰሰ፣ የተንገላታ፣ ጽኑ መከራን የተቀበለ፣ በሥቃይ ተሰቅሎ የሞተው አንዱ ጌታ ለፍቅር ነውና!

ድንቅ በሆነው ፍቅሩ ስቦ ተገዚዎቹ ያደረጋቸው የፍቅር ምርኮዎች ለፍቅር የሞተውን ጌታ በፍጹም ልባቸው፣ በፍጹም ነፍሳቸው፣ በፍጹም ኃይላቸው ወደዋል፡፡ (ማቴ.፳፪፥፴፯) ከራሳቸውም አልፎ ሰውን በፍጹም ልባቸው በመውደድ እጅጉን በሆነ ብዙ ሥቃይ እርሱን መስለው ተገኝተዋል፡፡ እውነትን ወደው ሐሰትን ጠልተዋልና፤ ከምድር ተድላ ይልቅ ሥጋዊ መከራን ፈቅደዋልና፤ ለፍቅር ሲሉ ተርበዋልና፤ ተጠምተዋልና፤ ተራቁተዋልና፤ ተሰደዋልና፤ ተንገላትተዋልና፤ ተሠቃይተዋልና፤ በግፍ ተድገለዋለና የፍቅር ምርኮዎች በመጨረሻ ያበራሉ!

ጸአር፣ ገአርና ኀሣር በሞላበት በዚች ጨለማ ዓለም፣ የምድራዊ ከንቱነት ታክቷቸው፣ ብርሃን የሆነውን ወንጌል በተስፋ ሰንቀው በጽድቁ ጎዳና በሚጓዙበት ጊዜ የሚመጣባቸውን ሥቃይ ስለ ፍቅሩ የሚቀበሉ ቅዱሳን በነጻ ፈቃዳቸው ለጌታ የሚገዙ የፍቅር ምርኮዎች ናቸው፡፡ በክርስቶስ ፍቅር የተንገበገቡ፣ ልባቸው የተቃጠለ፣ አንጀታቸው የተንሰፈሰፈ አፍቃሪዎቹ ናቸው፡፡

ዕለት ዕለት ስለ እርሱ ይገፋሉ፤ እውነትን ስለመሻታቸው ስደት ልማዳቸው ነው፤ ከሐድዲያንን ጠልተው ጽድቅን ይራባሉ፤ ቀን በበረኃ ውእየት፣ ማታ በጨለማ ቁር ይሠቃያሉ፡፡ በዱር ገደል መሽገው ዘወትር አምላካቸውን ያገለግላሉ፡፡ ይህን ሁሉ ስለ ጌታ ፍቅር አደረጉት!

ፍቅር እውነት በመሆኑም የእውነት ምስክሮች ሆኑ፤ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ‹‹ሰማዕታት የዚህችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ፡፡ ስለ እግዚአብሔር ደማቸውን አፈሰሱ፡፡ ስለ መንግሥተ ሰማያትም መራራ ሞትን ታገሡ›› በማለት እንደተናገረው ክሕደትና ሐሰት፣ ስርቆትና ንጥቂያ፣ ማስመሰልና ከንቱነት በበዛበት በዚች ውጥንቅጥ ዓለም ውስጥ ሲኖሩ፣ ሲገፉና ሲበደሉ ትዕግሥትን ገንዘብ አድርገው፣ በጽናት በጨለማ ውስጥ እንደ ሻማ አበሩ፡፡  (ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ) በዋሻ ሆኖ እንደሚለኮስ ጧፍ፣ በድቅድቅ ጉድጓድ ውስጥ እንዳለ ፋኖስ፣ በጠባብና ትንሽ ደሳሳ ጎጆ እንደሚያበራ መብራት ሆነው ደመቁ፡፡

ቀጥተኛ በሆነችው አንዲት ርትዕት ሃይማኖት፣ ለአንድ እውነተኛ አምላክ የመገዛታቸው ምስክር የክርስቶስን መከራ መስቀልም ስለ መሸከማቸው፣ ብርሃን የሆነው ጌታ በላያቸው ያበራል፡፡ ሕይወታቸው በሙሉ እርሱን በመፍራትና በመታዘዝ፣ ስለ ፍቅሩ ሲሉ ራሳቸውን ጥለው፣ ቤተ ሰቦቻቸውን ትተው፣ ቀያቸውን ለቀው፣ በስደትና በእንግልት መኖርን ስለፈቀዱ ብርሃን የሆነው አምላክ አይለያቸውምና፡፡

መላ ቅጡ በጠፋባት በዚህች መራራ ዓለም እንደ ጨው ሆነው ያጣፍጣሉ፡፡ ሐሰተኝነት ሲበዛ እውነት እንዳይጠፋ፣ ፍርድ ሲጓደል ፍትሕ እንዳይረሳ፣ ጥላቻ በሕዝብ መካከል ሲሠርጽ ፍቅር እንዳይጠፋ ምስክሮች ይሆናሉ፡፡ ስለት ሳያስፈራቸው፣ የጥፋት ሰንሰለት ሳያስራቸው፣ ሥቃይ ሳይበግራቸው ከጠላት ጋር ፊት ለፊት ተጋፍጠው እውነተኛ ስለሆነው ፈጣሪ መስክረዋል፤ ከፍቅሩም የተነሣ ጽኑ ግርፋትን ተቀብለዋል፤ ቆዳቸውን ተገፈዋል፤ በብረት መጋዝ ተቆርጠዋል፤ በፍል ውኃ ተቀቅለዋል፤ በእሳት ተቃጥለዋል፤ ‹‹….እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ሌሎችም መዘባበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ›› እንዲል፡፡ (ዕብ.፲፩፥፴፭)

ዘወትርም ቀራንዮን በማሰብ የጌታን ሥቃይ በእምነት መነጽር እየተመለከቱ በሚያቃጥል እንባ ልቅሶን ያበዛሉ፤ የተገረፈውን ግርፋት በማሰብ ጀርባቸውን ተገርፈዋል፤ ፊታቸውን በጥፊ ጸፍተዋል፤ ከፍቅሩ ብዛት ራሳቸውን ከቆጥና ዛፍ፣ ከድንጋይም ራሳቸውን ወርውረዋል፤  ሞተዋል፡፡ ድንቅ በመሆነው ተአምራቱ እርሱ ደግሞ ያስነሣቸዋል፤ ይፈውሳቸዋልም፡፡ (ገድለ አቡነ አቢብ)

የፍቅር ምርኮዎች የፍቅር ተገዢዎች ስለመሆናቸው በበጎ ፈቃዳቸው በነጻነት ለሚገዛ አምላክ በፍጹም ፍቅር አምልኮት ይፈጽማሉ፤ ኑሮአቸውም ሆነ ውሎአቸው፣ በፍሪሃ እግዚአብሔር መኖርን ይመርጣሉ፡፡ እርሱ መመኪያቸው ነውና ስለምንም ምን አይጨነቁም፤ አይፈሩምም፡፡ ጋሻ መከታቸው፣ ኃይል ብርታታቸው፣ ጽናት ተጋደሎአቸው አንድ ፈጣሪ ነውና፡፡ ልብሳቸውም ይሁን ምግብ መጠጣቸው እርሱ ነውና፡፡

በችግር ጊዜም ቢሆን መሻገሪያ ድልድያቸው፣ በመራቆት ሰዓት የጽድቅ ልብሳቸው፣ በመራብ ጊዜ ምግባቸው እርሱ ነው፡፡ የዘለዓለማዊ መብልና መጠጥን የሚያድል ኤልሻዳይ አምላክ የመሆኑን ምሥጢር በሚገባ የተረዱ ናቸውና ስለ ሥጋዊ መራብና መጠማት አይጨነቁም፡፡ እውነተኛ ሕይወትን የሚሰጥ ጌታ ለዘለዓለም በፍቅሩ ጠብቆ በሰላምና በነጻነት እንደሚያኖራቸው ፍጹም እምነት ያላቸው በመሆናቸው ሰማይና ምድር ለፈጠረ አንድ አምላክ ተገዝተው መኖርን የመረጡ ናቸው፡፡ በመጨረሻም ስለ ፍቅሩ በመሞት፣ መንግሥቱን በመውረስ ለዘዓለም ከእርሱ ጋር በተድላ ደስታ ይኖራሉ፡፡

የሰማዕታት የቅዱሳን ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ በረከታቸው ይደረብን፤ አሜን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

በአታ ለእግዝእትነ ውስተ ቤተ መቅደስ

ከደጋጎቹ ቅዱሳን አባቷና እናቷ ኢያቄምና ሐና የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ቀን የከበረ ነው፡፡ በበጎ ምክር በእግዚአብሐርም ፈቃድ ይህ ሆነ፤ በዚያን ጊዜ ኢያቄምና ሐና “….ሆዷ ዘመድ ሳይወድ አፏ እህል ሳይለምድ ወስደን እንስጥ” ብለው በመማከር መባዕም ጨምረው ወደ ቤተ መቅደስ ሄዱ፡፡   

ተዝካረ ልደቱ ለኤልያስ ነቢይ

ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ቅዱሳት መጻሕፍት ነቢዩ ኤልያስ የተወለደው በታኅሣሥ ፩ ቀን ከነገደ ሌዊ እንደሆነ ይገልጻሉ፤ የአባቱ ስም ኢያስንዩ የእናቱ ስም ቶና ይባላሉ፡፡ በተቀደሰች የልደት ቀኑም አባቱ ብርሃን የለበሱ አራት ሰዎች ሲሰግዱለትና ሕፃናት በሚጠቀልሉበት ጨርቅ ፈንታ በእሳት ሲጠቅልሉት  ተመልክቷል፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ዘኅዳር ፩፣ መዝገበ ታሪክ ገጽ ፹፬)

ኢትዮጵያ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተአምኆ ቅዱሳን መጽሐፉ ስለዚሁ ነቢይ እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ “ቴስቢያዊ (የቴስቢያ ሰው)፤ ኮሬባዊ (ወደ ኮሬብ ተራራ የወጣ)፣ ታቦራዊ (በታቦር ተራራ የተገኘ)፣ ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን የለጐመ ለሆነ፣ የጸሎቱ ቃልም በአዶናይ ዦሮ ውስጥ ለተሰማ፣ ውኃውን እስኪበላ ደርሶ እሳትን ከሰማይ ያወረደ ለሆነ፣ በእሳት ሠረገላ ተጭኖ ወደ ተድላ ደስታ ቦታ ለገባ ለነቢዩ ለኤልያስ ሰላምታ ይገባል።”

ሊቁ አርከ ሥሉስም በአርኬ መጽሐፉ ላይ ደግሞ እንዲህ ብሏል፤ “ምድራዊ የሆነ የዓለም ሕይወትን አራግፈህ ለማረፍ ወደ ሰማያት ያረግህ ለሆንክ ለአንተ ለኤልያስ ሰላም እላለሁ፡፡ አክአብን ለተናቀ ሥራው እየዘለፍከው ጣዖታትን የቀጠቀጥክ ማምለኪያዎቹን ያፈረስክ በምስጋናህ ምንኛ ተመሰገንህ።”

ቅዱሱ መጽሐፍ የዚህን ፈፍ  ነቢይ ስም “ኤልያስ” ፻ (መቶ) ጊዜ ጠቅሶታል፡፡ ድንቃ ድንቅ ተአምራቱንም መዝቦት እናገኛለን፤ ከእነዚህም መካከል አክአብና ኤልዛቤል ጣዖት በማምለከታቸው ኤልያስ ሦስት ዓመት ከ ስድስት ወር ዝናብን በጸሎቱ አቁሟል፡፡ (፩ኛ ነገ. ፲፯)፤ የሰራጵታዋን መበለት የሞተ ልጇን አስነሥቷል፡፡ (፩ኛ ነገ.፲፯፥፲፱)

ለአምላካችን እግዚአብሔር ያቀረበውን መሥዋዕት እሳት ከሰማይ ወርዶ የበላለት ነቢይ እንደሆነም መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፤ (፩ኛ ነገ ፲፰) ከሦስት ዓመት ከስድስት ወር በኋላ ቀርሜሎስ ወጥቶ በመጸለይ ዝናብ እንዲዘንብ አድርጓል፤ (፩ኛ ነገ. ፲፰) አካዝያስ የላካቸውን ፶ (ኀምሳ) አለቃዎች እሳት ከሰማይ አውርዶ አቃጥሏል፤ (፪ኛ ነገ. ፩) በመጐናጸፊያው የዮርዳኖስን ወንዝ ከፍሏል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፬) በእሳት ሠረገላ በዐውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጥቷል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፩)፣ በደብረ ታቦር ጌታ ምሥጢረ መንግሥቱን ሲገልጽ ከሙሴ ጋር ዐብሮ ተገኝቷል፤ (ማቴ.፲፯፥፬) ዳግመኛ በመምጣት በሐሳዌ መሲሕ ጊዜ ሰማዕትነትን ይቀበላል፡፡ (ማቴ.፲፯፥፲፩)

የነቢዩ ኤልያስ በረከት ይደርብን!

 

ሥዕለ አድኅኖ

 ክፍል ሦስት

ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ 

ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁ? እንኳን ለጾመ ነቢያት (የገና ጾም) አደረሳችሁ! ይህ ጾም የሚጾመው አባቶቻችንን ነቢያት እግዚአብሔር በሰጠን ተስፋ በገባልን ቃል ኪዳን መሠረት ከሰማያት ወርዶ እንዲያድነን “አቤቱ ውረድ፤ ተወለድ፤ አድነን” እያሉ የጾሙት ጾም ነው፤ እኛ ደግሞ ከሰማያት ወርዶ፣ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ አድኖናል እያልን ውለታውን እያስታወስን እንጾመዋለን፡፡ ከሰባቱ የዐዋጅ አጽዋማት አንዱ ስለሆነ እኛም እንደ አቅማችን ልንጾመው ይገባል! መልካም!

ትምህርታችሁንም በርትታችሁ ተማሩ! የመንፈቀ ዓመቱ ፈተናም እየተቃረበ ነው፤ በደንብ በማጥናት ጥሩ ውጤት ማስመዝገብ አለባችሁ! በሰንበት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መማርን፣ማገልገልንም እንዳትረሱ።

ባለፈው ትምህርታችን ስለ ሥዕለ አድኅኖ በተማርነው ትምህርት ሥዕለ አድኅኖ እንዴት መሣል እንዳለበት በመጠኑ ተምረናል፡፡ ዛሬ ደግሞ ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል የምንጠቀማቸው ቀለማት (ከለር) ምን ዓይነት መሆን እንዳበቸውና ምክንያቱን የተወሰኑትን ለአብነት እንመለከታለን፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለቅዱሳት ሥዕላት የምንጠቀማቸውን የቀለማት ውክልና ከማየታችን በፊት ቀለም ምንድን ነው የሚለውን እንመልከት፤ ቀለም የሚለውን ሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ የቃላትን ፍቺ (ምሥጢር) በተረጎሙበት መጽሐፋቸው ቀለም በቁሙ “ኅብር፣ ፈሳሽ፣ ዓይነት፣ መጣፊያ፣ ማቅለሚያ” ብለው አብራርተውታል፡፡ (ኪዳነ ወልድ መዝገበ ቃላት ገጽ ፯፻፺፫/793)

ቀለማት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ሥዕለ አድኅኖ ሲሣሉ የሚያስተላልፉት መልእክትም አላቸው፤ የፈጣሬ ዓለማት የቅድስት ሥላሴ፣ የእመቤታችን ቅድስት ደንግል ማርያምን፣ ሥዕል ሲሣል የሚቀባው ቀለም ዓይነት የራሱ የሆነ ትርጒምና የሚያስተላልፈው ነገር አለው፤ የቅዱሳን መላእክትን፣ የቅዱሳን አበውን፣ የቅዱሳት እናቶችን ሥዕልም በሚሳልበት ጊዜ የተጋድሏቸውን ጽናት፣ የክብራቸውን ዓይነት፣ የመጠሪያ ስያሜአቸውን ለመለያነትም ያገለግላል፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! የቅዱሳን ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል በሥዕሉ ባለቤት በራሱ           ዙሪያ በክብ ቅርጽ ጸዳለ ብርሃን (አክሊለ ብርሃን) ተደርጎ ይሣላል፤ በዚህም ለመግለጽ የተፈለገው ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያን የቅድስና ማዕረግ እንደተሰጣቸው ለመግለጽ ነው፡፡

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ክቡ ቅርጽ በቅድስት ሥላሴና በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሥዕለ አድኅኖ ላይ የሚደረገው ጸዳለ ብርሃን የእግዚአብሔር ቅድስና የባሕርይው መሆኑን ለመግለጽ ነው፡፡ ለቅዱሳን ሲደረግ ደግሞ አምላካችን የባሕርይ ቅድስናውን መልካም በመሥራታቸው በጸጋ (በስጦታ) ለቅዱሳን ቅድስናን እንደሰጣቸው ለመግለጽ የቅዱሳት ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል በራሳቸው ዙሪያ በብርሃን ክብ ቅርጽ ይደረግላቸዋል፡፡

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! በቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና መሠረት አብዛኛውን ጊዜ የምንጠቀማቸው ቀለማት ነጭ፣ ሰማያዊ፣  ቢጫ፣ አረንጓዴና ቀይ ሲሆኑ ቀለማቱ ራሱን የቻለ ምሥጢር ወይም ትርጒም አላቸው፡፡

 ነጭ፡- የድል አድራጊነት፣ የንጽሕና እና የፍጹምነት ምሳሌ ነው፡፡ ቅዱሳን ዓለምንና ምኞቱን ድል ያደረጉ ልበ ንጹሐን በመሆናቸው ነጭ ልብስ ለብሰው ይሣላሉ፡፡ እንዲሁም ደግሞ መለኮታዊ ክብርንም ያሳያል፡፡ ለምሳሌ በደብረ ታቦርና በትንሣኤ ሥዕሎች ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነጭ ልብስ ለብሶ ይሣላል፡፡ (ኦርቶዶክሳዊ ቅዱሳት ሥዕላት ገጽ ፸፬)

ሰማያዊ፡- ሥዕለ አድኅኖ ሲሣሉ ሰማያዊ ቀለምን መቀባቱ በመልካም ሥራው ሰማያዊውን ሀብት (መንግሥተ ሰማያትን) ገንዘብ ለማድረግ (ለመውረስ) አባቶቻችን ቅዱሳን በፈቃደ ነፍስ ለመመራት መልካም ሥራን ለመሥራታቸው፣ ኃጢአትን መጥላታቸውን ለሰዎች መልካምን ማድረጋቸውን ለማመልከት እንዲሁም በመንፈስ ፍሬዎች በተባሉ በትዕግሥት፣ በትሕትና፣በፍቅር፣ በደስታ፣ በእምነት፣ በቸርነት (ገላ. ፭፥፳፪) ፈቃደ ሥጋን (ክፉ ምኞቶችን ሁሉ ድል ማድረጋቸውን ለማመልከት ለሥዕለ አድኅኖ ሲሣሉ ይህንን ቀለም እንጠቀመዋለን፡፡ሌላው ደግሞ ከቁጣ፣ ከቂም፣ ከበቀል ርቀው በትሕትናን ለመኖራቸው ምሳሌ ነው፡፡

 ቢጫ፡- ይህ ቀለም እውነተኛነትንና ብርሃንነትን ይገልጻል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትምህርቱ ‹‹እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ …›› (ማቴ.፭፥፲፬) በማለት እንዳስተማረው በመልካም ሥራቸው ለሌላው ብርሃን የሆኑትን ቤተ ክርስቲያን የቅድስና ማዕረግ ላይ የደረሱትን ቅዱሳን እውነተኞችና የዓለም ብርሃን ናችሁ ስትል በራሳቸው የብርሃን አክሊል በቢጫ አድርጋ ትሥላለች፡፡

አረንጓዴ፡- ከልምላሜና ከጸዳል ጋር ስለሚያያዝ መንፈሳዊ ትርጒሙ መታደስን አዲስ ሕይወት፣ ደኅንነትና ተስፋን ያሳያል፡፡ በዚህ መሠረት በትንሣኤ በአዲስ ሕይወት እንደምንኖር ያመለክትልናል፤ አረንጓዴነትና ሕይወት ተወራራሽ ይሆናሉ፡፡

 ቀይ፡- ሥዕለ አድኅኖ  ሲሣሉ በቀይ ቀለም መሳላቸው ሰማዕትነትን ያሳያል፤ ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውያን ምእመናን በላከወ መልእክቱ ‹‹…በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፣ ተፈተኑ በመጋዝ ተሰነጠቁ፣ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ …›› (ዕብ.፲፩፥፴፮) በማለት እንደገለጸው ስለ ሃይማኖታቸው መከራ የተቀበሉትን ሰማዕት የሆኑትን ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን ሥዕለ አድኅኗቸው በቀይ ቀለም ይሣላል፤ ቅዱሳን ነፍሳቸውን ለመከራና ለሞት አሳልፈው ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርስቲያን ብለው መስጠታቸውን ለማመልከት ይህንን ቀለም እንጠቀመዋለን፤ እንዲሁም ቀይ ቀለም የነጻ አውጪዎችም ምልክት ተደርጎ ይወሰዳል፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለዛሬ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሐዶ ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል ምንን ዓይነት ቀለማት እንደምንጠቀም በመጠኑ ለአብነት ተመልክተናል፤ በቀጣይ በሥዕለ አድኅኖ የተደረጉ ተአምራት እንማራለን፤

ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ በዘመናዊ ትምህርታችሁ በርትታችሁ ተማሩ ለወላጅ መታዘዝን፣ ለሰዎች መልካም ማድረግን እንዳትረሱ፤ በሰንበት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መንፈሳዊ ትምህርትንም ተማሩ፡፡ ቸር ይግጠመን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

 

ትሩፋን

ኀዳር ፳፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

 ቅዱሱ መጽሐፍ ትሩፋን ከጦርነት፣ ከስደት፣ ከምርኮ የተረፉትን ሰዎች እንደሚያመልክት ይነግረናል፡፡ “ትሩፍ” ጥሬ ቃሉ “የቀረ፣ የተረፈ፣ ቀሪ፣ ትርፍ” የሚል ትርጓሜ አለው፡፡ (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ፣ ገጽ ፱፻፫) ናቡከደነፆር እስራኤልን ወደ ባቢሎን ማርኮ ከወሰዳቸው ከሰባ ዘመን በኋላ በባቢሎን የቀሩት ከተማረኩት ሽማግሎች ትሩፋን ይባላሉ። በንጉሡ ዘመነ መንግሥት ከኢየሩሳሌም ተማርከው ሰባ ዘመን በፋርስ በባቢሎን የሚኖሩ የእስራኤል ሕዝብ ትሩፋነ ባቢሎን እንደሆኑም መጽሐፍ ያስረዳናል። (ዕዝራ ፪፥፩)

በተለያዩ ዘመናት በአንድም በሌላ ምክንያት በሰዎች፣ በጎሳ፣ በማኅበረሰብ ዘንድ እንዲሁም በሀገራት መካከል በሚከሰት ጦርነት እልቂት አልያም የግፍ ግድያና ጭፍጨፋ የተነሣ የብዙዎች ሕይወት ይጠፋል፤ ታሪክ ለዚህ ቀደምት ምስክር እንደሆነ የምናውቀው እውነት ነው፡፡ የጦርነት ወሬ ደግሞ ለእኛ አዲስ የሆነ ነገር አይደለም፡፡ እራሱ ጌታ በወንጌል ሲናገር  ‹‹ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፤ አትደንግጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው። ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣልና፥ ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል›› እንዳለው ምድር ላይ እነዚህ ሁሉ መከራዎች እየተከሰቱ እንደሆነ ለማንም የተደበቀ አይደለም፡፡ (ማቴ.፳፬፥፮-፯)

ታዲያ የጦርነት አስከፊ ገጽታው እንጂ መልካም ጎኑ ምን አልባት እርሱ ባወቅና በፈቀደ ጠላትን ከሀገር የማስወጣቱ ተግባር ነው፡፡ በዚህም አብዛኛዎቻችን ጦርነትን በውዴታ ሳይሆን በግዴታ የምንቀበለው ነው፡፡ ከሁሉም አስከፊው ደግሞ ቤተሰቦቻቸውን፣ ዘመድ አዝማዳቸውንና ወዳጆቻቸውን የሚያጡ ትሩፋን የሚገጥማቸው ሥቃይና ጉዳት ነው፡፡ በአንድ በኩል ከአሰቃቂ ግድያ አልያም ከሞት መትረፍ ቢያስደስትም በሌላ በኩል ግን የሚወዱትን ማጣት እጅግ አስከፊ ነው፡፡ ከምንም በላይ ግን የሞት ሞት የሆነው የነፍስ ሞት አሰቃቂ ነው፡፡

ሰዎች ሞትን እንፈራለን፤ የሥጋ ሞት አስጨናቂ እንደሆነ ማንም የማይክደው ሐቅ ነው፡፡ ነገር ግን ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ኢትፍርህዎ ለሞት፤ ፍርህዋ ለኃጢአት፤ ሞትን አትፍሩ፤ ኃጢአትን እንጂ›› ይለናል፡፡ ሊያስጨንቀን የሚገባው በኃጢአት ምክንያት የሚመጣብንን የነፍሳችን ሞት እንጂ የሥጋ ሞት ሊሆን እንደማይገባ በዚህ ቃል እንረዳለን፡፡ ‹‹አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ›› በሚለው አምላካዊ ቃል ሥጋዊ ሞት አይቀሬ በመሆኑም ምንም ለማንቀይረው  ነገር መጨነቁ ጥቅም የለውም፡፡ (ዘፍ.፫፥፲፱) 

የነፍስ እንጂ የሥጋ ጦርነት ትሩፋን ባንሆን እጅጉን ይመረጣል፡፡ ቃሉን ተረድተው፣ በሕጉ ኖረው ትእዛዙን የጠበቁ ጻድቃን ሁሉ በነፍሳቸው አትርፈው ከዚህ ዓለም ድካምና ዕረፍት በክብር እንደተለዩ ቅዱሳት መጻሕፍት ምስክር ናቸው፡፡ (ገድለ ቅዱሳን) አብነት መሆናቸውን ደግሞ በክርስቶስ ክርስቲያን የተባልን የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ሁላችን ማወቅ አለብን፡፡   እውነት ስለሆነው አንድ ጌታና አንዲት እውነተኛ ሃይማኖት ሲሉ መከራን በመቀበል በቀናው መንገድ ተጉዘው መልካም ፍሬን ያፈሩ ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት የነፍስ አትራፊዎች/ትሩፋን/ ናቸው፡፡

የልባችን መሻት የሁላችንም ምኞት መሆን ያለበት ይህ ነገር ሆኖ ሳለ፣ በመንፈስ ውጊያ ለማሸነፍ የሚያስችለንን ስንቃችንን ደግሞ ማከማቸት አስፈላጊ በሆነበት ሰዓት፣ እኛ ግን እየተጨነቅን ያለነው በጊዜያዊ ችግርና ወቅታዊ የእርስ በርስ ጦርነት ላለመሞት ነው፡፡ የሥጋዊ ሞትን ፈርተን በምንዘናጋበት ጊዜ ግን ነፍሳችንን እንደ አንበሳ ነጥቀው ሊጥሏት ይችላሉና ይህንን እንፍራ!

ነፍስ ዘለዓለማዊ ስትሆን ሥጋ ግን ጊዜያዊ ነው፤ አላፊ ጠፊ የሆኑ ምድራዊ ነገሮችን ለሟሟላት በሚል በምድር ለመኖር ስንሻ ከሁለት ያጣም የመሆን ሁኔታ ሊኖር ስለሚችል መጠንቀቅ ይገባል፡፡ ስለ ሥጋዊ ሞት ስናስብ መንፈሳዊ ዝለት ያጋጥመናል፤ በዚህም ጊዜ ነፍሳችን ትጎዳለች፤ ታድፋለች፤ ትመነምናለች፡፡

ሰው ጦርነትን ፈርቶ ሊሸሽ ይችላል፤ መሰደደም ሆነ መደበቅም አይከፋም፤ ግን ግልጽ የሆነውን አስከፊ ሁኔታና እየተካሄደ ያለውን ጦርነትም ይሁን እልቂት ማስቆም ካልተቻለ ሃይማኖታችን በሚፈቅድልን ተገቢ መንገድ ድምጻችንን ማሰማቱና መልእክት ማስተላለፍ እንጂ የጠላት ወገን ከሆኑ አካላት ጋር ግብ ግብ መፍጠር አልያም ጦርነት ውስጥ መግባት አላስፈላጊ ነው፡፡ ጠላት ፊት ለፊት መጥቶ ሊገለን ቢፈልግ እንኳን “ማኅተባችንን አንበጥስም” ብለን አንገታችንን ለሰይፍ ሰውነታችንን ለሞት አሳልፈን መስጠት ሰማዕትነት ነው፤ የክብር ሞትም ያሰጠናል፡፡

በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተለይም በዕረፍት በዓሏ በየወሩ ፳፩ ቀን የሚነበበው መልክአ ማርያም ‹‹ኃጥአን ከታላቅ የደስታ አደባባይ በተሰደዱ ጊዜ ምርኮ እሆንሽ ዘንድ ከእነርሱ ለይተሽ አስቀሪኝ›› ይለናል፡፡ (መልክአ ማርያም) ይህ ድንቅ ጸሎት የሚያመለክተን ከጦርነት ምርኮኝነት ለማምለጥ ማቀድ ሳይሆን ከኃጥአን ጎራ ላለመቆጠር መሻት እንዳለብን እንዲያውም የፍቅር ምርኮ መሆን እንደሚገባ ነው፡፡

ንጽሕት ቅድስት ከምትሆን የአምላክ እናት የተለመነው ይህ መማጸኛ ለሁላችን እንደሚሆን  እናምናለን፡፡ የነፍሳችንን ጥፋት የማይፈልገው አምላካችን አንዲያ ልጁን አሳልፎ ሰጥቶ ያዳነን ክብርት በሆነች እናቱ ድንግል ማርያም ነውና ታማልደን፣ ትለምንልን እና ትራዳን ዘንድ መማጸን የተገባን ነን፡፡ ከጠላት ሰይጣን የመንፈስ ውጊያ እንድታተርፈን፣ ምርኮዎቿ  እንድታደርገንን እንለምናት፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!