ርእሰ ዲያቆናት ወቀዳሚ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ

ጥቅምት ፲፯፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ርእሰ ዲያቆናት ወቀዳሚ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ የሹመቱ መታሰቢያ ጥቅምት ፲፯ ነው፡፡ ከሰባቱ ዲያቆናት መካከል ቀዳምት የሆነው ቅዱሱን የመረጡት እራሳቸው ሐዋርያት ናቸው፡፡ የስሙ ትርጓሜ “ፋና፣ አክሊል” የሆነ የእግዚአብሔር ልዩ ባለሟል፣ አጋእዝተ ዓለም ሥላሴን በክብሩ ለማየት የበቃ ሰማዕትም ነው፡፡

ፍጹም እምነት ያለው፣ መንፈሳዊ ቅናትን የተመላ እንዲሁም ተአምር የማድረግ ጸጋ የነበረው ቅዱስ ነበረ፡፡ በዘመኑ የሚያስተምራቸው ትምህርቶችም ሆነ ንግግሮቹ መንፈስ ቅዱስ የመላባቸው ስለነበሩ በመቃወም ይከራከሩት የነበሩትን ሁሉ መልስ አሳጥቶአቸዋል፡፡ በዚህም ነበር በቅንአት ተነሣሥተው በሐሳት ምስክር የከሰሱት፡፡ በኋላም ተፈርዶበት በድንግይ ተወግሮ የሰማዕትነትን አክሊል በተወለደበት ዕለት ጥር አንድ ቀን ተቀብሎአል፡፡

የቅዱስ እስጢፋኖስ ጸሎት፣ አማላጅነት እና ተራዳኢነት አይለየን፤ ከበዓሉ በረከት ያሳተፍን፤ አሜን!

ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ

ጥቅምት ፲፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

የቊስጥንጥንያ ንጉሥ የቴዎዶስዮስ ልጅ የቅዱስ ገብረ ክርስቶስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው ጥቅምት ፲፬ የከበረ በዓል ነው። ቴዎዶስዮስ የተባለው ንጉሥ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው፤ ሚስቱም በጎ የምትሠራ እግዚአብሔርንም የምትፈራ ናት፤ ስሟም መርኬዛ ነው። እነርሱም ልጅ ስለሌላቸው ያዝኑ ነበር፤ ወደ ኢየሩሳሌምም ሒደው ስእለትን ተሳሉ፤ ቸር መሐሪ ወደሆነ እግዚአብሔርም ለመኑ፤ እርሱም ልመናቸውን ተቀበሎ ይህን ያማረ ልጅ ሰጣቸው፤ ስሙንም አብደልመሲህ ብለው ሰየሙት፤ ትርጓሜውም ገብረ ክርስቶስ ማለት ነው። የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ የሥጋዊንም ትምህርት አስተማሩት።

አድጎ በጕለመሰም ጊዜ የሮሜውን ንጉሥ ልጅ አጭተው እንደ ሥርዓቱ አጋቡት ከሌሊቱ እኩሌታም በሆነ ጊዜ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ተነሥቶ ወደሙሽራዪቱ ገባ፤ እጅዋንም ይዞ ከእርስዋ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ ። ከዚያም የሃይማኖት ጸሎት በአንድ አምላክ እናምናለን የሚለውን እስከ መጨረሻ ጸለየ፤ የተሞሸረበትንም ልብስ ከላዩ አውልቆ የግምጃ ልብስን ለበሰ፤ ወደ ሙሽሪቷም ሒዶ ራስዋን ሳማት፤ እንዲህም እያለ ተሰናበታት፤ “እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኑር፤ ከሰይጣን ሥራ ሁሉ ያድንሽ።” እርሷም አልቅሳ “ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ? ለማንስ ትተወኛለህ? አለችው፤ እርሱም “በእግዚአብሔር ዘንድ እተውሻለሁ፤ እኔም ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን ልከተለው እሔዳለሁ፤ የአባቴ መንግሥት አላፊ ነውና አንቺም መሐላሽን አስቢ” አላት፤ ያን ጊዜ መሐላዋን አስባ ዝም አለች።

ለሠርጉም የታደሙት ሁሉ እንደተኙ በሌሊት ወጥቶ ሔደ፤ ወደ ባሕርም ዳርቻ ደርሶ በመርከብ የሚጓዙ መንገደኞችን አገኘ፤ የዓመት መንገድ ወደሚሆን አርማንያም እስከሚደርስ ከእነርሱ ጋር ተጓዘ።

ነግቶ ወደ ሠርጉ አዳራሽ አባትና እናቱ በገቡ ጊዜ ሙሽራውን ልጃቸውን አላገኙትም፤ ሙሽሪትንም “ልጃችን ወዴት አለ?” ብለው ጠየቋት፤ እርሷም እንዲህ አለቻቸው። “በሌሊት ወደ እኔ ገባ፤ መሐላን አማለኝ፤ ከእኔ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፤ ራሴንም ስሞኝ ከእኔ ዘንድ ወጣ፤ እኔም እያለቀስኩ ብቻዬን አደርኩ፤” ነገርዋንም ሰምተው ወድቀው በመጮህ ታላቅ ልቅሶን አለቀሱ።

በዚያችም ጊዜ በሀገሮች ውስጥ ሁሉ ልጁን ገብረ ክርስቶስን ይፈልጉት ዘንድ ንጉሡ አምስት መቶ አገልጋዮቹን ላከ፤ ለድኆችና ለምስኪኖችም ምጽዋት አድርገው የሚሰጥዋቸውን ብዙ ገንዘብን ሰጣቸው።

ገብረ ክርስቶስ ግን በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በአርማንም አገር በተሠራች በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ደጅ የሚኖር ሆነ። አባቱ የላካቸውም ሁለቱ አገልጋዮች ከዚያ ደርሰው ስለርሱ መረመሩ፤ ግን ወሬውን ማግኘት ተሳናቸው፤ ለድኆችም ምጽዋትን ሰጡ፤ እርሱም ከድኆችም ጋር ምጽዋትን ተቀበለ።

በዚያም ዐሥራ አምስት ዓመት ከኖረ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለአንድ ቄስ ተገለጸችለት፤ ቦታውንም አመልክታ እንዲህ አለችው። “የእግዚአብሔር ሰው ገብረ ክርስቶስን ይዘህ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስገባው፤ ከውጭ አትተወው፤” ቄሱም እመቤታችን እዳዘዘችው አደረገ።

ከዚህም በኋላ የተመሰገነ ገብረ ክርስቶስ በሌሊት ተነሣ ከእመቤታችንም ሥዕል ፊት ቁም ጸለየ፤ እንዲህም አላት፤ “እመቤቴ ሆይ የተሠወረ ሥራዬን አንቺ ለምን ገለጥሽ፤ አሁንም ወደሚሻለኝ ምሪኝ፤” ይህንንም ብሎ የእመቤታችንን ሥዕሏን ተሳልሞ በሌሊት ወጥቶ ወደ ባሕሩ ወደብ ደረሰ፤ ወደሌላ ሀገርም ሊሔድ ወዶ በመርከብ ተሳፈረ። ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ከአባቱ አገር ደረሰ የአባቱና የእናቱም ባሮች እየናቁትና እየሰደቡት በአባቱ ደጅ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ።

ሲገቡና ሲወጡም “ሽታው እንዳያስጨንቀን ይህን ምስኪን አስወግዱልን” ይላሉ፤ ወጭትና ድስትም አጥበው በላዩ ይደፉበታል፤ ውሾችም እንዲናከሱበትና እንዲበሉት የሥጋ ትርፍራፊ ይጥሉበታል፤ ውሾች ግን ቁስሉን ይልሱለት ነበር፤ እንደዚህም አብዝተው አሠቃዪት።

ከዚህም በኋላ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ለመነ፤ “ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ለአባቴና ለእናቴ ባሮች በደል እንዳይሆንባቸው ወዳንተ ውሰደኝ።” በዚያንም ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው። ከዚህም በኋላ ገድሉን ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ጻፈ፤ በእጁም ጨብጧት ዐረፈ።

በእሑድ ቀንም ሕዝቡ ሁሉና ካህናቱ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር በቅዳሴ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሳሉ የእግዚአብሔርን ሰው በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ቤት ፈልጉት የሚል ቃል ከሰማይ ሰሙ፤ በዚያን ጊዜ ሔደው በአረፈበት ቦታ አገኙት። በእጁም ውስጥ የተጨበጠ ክርታስን አዩ፤ ሊወስዷትም ሽተው መውሰድ ተሳናቸው።

በአንድነትም በጸለዩ ጊዜ እጁ ተፈትታ ወስደው አነበቧት፤ አባትና እናቱም ልጃቸው እንደሆነ አወቁ፤ ታላቅ ጩኸትም ሆነ፤ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ፤ አክብረውም ቀበሩት፤ መቃብሩም በሽተኞችን ሁሉ በመፈወስ ድንቆች የሆኑ ብዙ ተአምራትን የሚያደርግ ሆነ።

አምላካችን እግዚአብሔር በቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን።

መጽሐፈ ስንክሳር ዘጥቅምት ፲፬

የባሕረ ሐሳቡ ደራሲ ቅዱስ ድሜጥሮስ

ጥቅምት ፲፩፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ከምንባባት ዐውድ

አካሄዱን ሁሉ ከእግዚአብሔር ጋር ያደረገ፣ እርፍ አርቆ፣ ድኮ ታጥቆ፣ ወይን አጽድቆ የሚኖር፣ የቀለም ትምህርት ብዙም ያልነበረው ሰው ድሜጥሮስ በቅን ልቡናው መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት ባሕረ ሐሳብን የደረሰ ቅዱስ ሰው ነው፡፡ ጌታ ባረገ በ፻፹(180) ዓ.ም የእስክንድርያ መንበር ዐሥራ ሁለተኛ ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ተሹሟል። በሹመቱም ጊዜ በትህርምት ኗሪ ነውና አሁን አጽዋማትንና በዓላትን የምናወጣበትን ይህን የቁጥር ዘመን ባሕረ ሐሳብ ተገልጾለት ደርሶታል፤ ተናግሮታል፤ ተናግሮት ብቻም አልቀረም፤ ለሦስቱ ሊቃነ ጳጳሳት ለሮሙ በቅዱስ ጴጥሮስ መንበር ሥር ለነበረው ለአባ ፊቅጦር፣ በቅዱስ ዮሐንስ መንበር ሥር ለነበረው ለኤፌሶኑ ሊቀ ጳጳስ በቅዱስ ጴጥሮስ ካልእ ሥር ለነበረው ለአንጾኪያው መንበር ለቅዱስ መክሲሞስ ዐራተኛ፣ ለኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ለአባ አጋብዮስ ልኮላቸዋል። እነርሱም ሐዋርያት ከአስተማሩት ትምህርት ጋር አንድ ቢሆንላቸው ተቀብለው ኑረውበታል፤ አስተምረውበታል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፬፥፵፩፣ ስንክሳር ኅዳር ፲)

ባሕርን ዘመን ሲል የት ይገኛል ቢሉ “እስመ በመዳልው ተደለወ ዓለም ወበመሥፈርት ሰፈራ ለባሕር፤ ዓለም በመስፈሪያ ተሰፍሯልና ባሕርንም በመስፈሪያ ሰፈራት” እንዳለ ዕዝራ (ዕዝራ ፪፥፴፯) ቅዱስ ዳዊትም “ዛቲ ባሕር አባይ ወረሐብ፤ ይህች ባሕር ታላቅና ሰፊ ናት” ብሏል፡፡ (መዝሙረ ዳዊት ፻፫፥፳፭) ሐሳብንስ ቁጥር ሲልስ የት ይገኛል ቢሉ ለትኩነኒ ሐሳበ ብላለች ኦሪት፡፡ ነቢዩ ዳዊትም “ብፁዓን እለ ተሐድገ ሎሙ ኃጢአቶሙ ወእለ ኢሐሰበ ሎሙ ኲሎ ጌጋዮሙ፤ መተላለፉ የቀረችለት ኃጢአቱም የተከደነችለት ምስጉን ነው” ብሏል፡፡ (መዝሙረ ዳዊት ፴፩፥፩) ይህን የመሠለው ሁሉ ብዙ ነው። አንድም እንዳለ ባሕረ ሐሳብ ይለዋል፡፡ ባሕር አለው ባሕር እስኪለምዱት ያስፈራል። ከለመዱት በኋላ ግን ዘግጦ ጠልቆ ግጫውን ጭንጫውን ይዞ እስከመውጣት ይደረሳል፡። ይህም ባሕረ ሐሳብ እስኪለምዱት ያስፈራል፡፡ ከለመዱት በኋላ ግን በዓላትን አጽዋማትን አወጣጣቸውን ብቻ ሳይሆን ኢይዐአርግ ኢይወርዳቸውን ሠርቀ መዓልታቸው ሠርቀ ሌሊታቸውንም ያሳውቃልና።

ነገር ግን ከእርሱ በፊት አጽዋማት አይጾሙም፤ በዓላት አይውሉም ማለት አይደለም። ከእርሱ በፊት ገና በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ሳሉ ከምእመናን ጋር ጾምን ይጾሙ፣ ትንሣኤንም ያከብሩ ነበር። ጌታ አርባ መዓልት አርባ ሌሊት የጾመውን ሥጋ ቅቤ አንቅመስ እንጂ እየዋልን እህል ውኃ ብንቀምስ እዳ እንደማይሆን ትንሣኤንም በመጋቢት በ፳፱ (29) ያከብሩ የነበረውን ከእሑድ አይውጣ እንጂ በሚያዝያ ይሁን ተለይቶ የነበረ ሰሙነ ሕማማት በአንድ ላይ እንዲሆን ያደረጉ ሐዋርያት ናቸው።

አበዊነ ሐዋርያት አፍለስዎ ለጾመ አርብዓ ወአስተላጽቅዎ ምስለ ጾመ ሕማማት፤ አባቶቻችን ሐዋርያት ተለይቶ የነበረውን አርባ ጾም ከጾመ ሕማማት ጋር አንድ አድርገውታል” እንዳለ አቡሻክር። አቆጣጠሩን ግን ለስብከተ ወንጌል ይፋጠኑ ስለነበር አንድም ወደፊት ድሜጥሮስ እንደሚነሣ በመንፈስ ቅዱስ አውቀው ለይተው አላስተማሩም። ከሐዋርያትና ከ፸(70) አርድዕት በኋላ የተነሡ መምህራንም እንዲሁ ከዘመን ብዛት የተነሣ ዕለቱ ቢጠፋባቸው ዐቢይ ጾምን የጥምቀት ሳኒታ ጥር ፲፩(11) ቀን ጀምረው በየካቲት ፳(20) ቀን ፈጽመው በዓልን ሳይሹ ያከብሩ ነበር። በዓላትን ሲሹ ደግሞ ሰሙነ ሕማማትን በመጋቢት ፳፪(22) ቀን ጀምረው በመጋቢት ፳፰(28) ቀን ፈጽመው በ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ትንሣኤን ያከብሩ ነበር። ከዚህም የተነሣ ዐቢይ ጾም ከእሑድ ውጭ በሌሎችም ቀን ሰኞም ማክሰኞም ይውል ነበር። በዚህ መንገድ ሲያያዝ መጥቶ ከቅዱስ ድሜጥሮስ ደርሷል። ይህም ድሜጥሮስ ከላይ እንዳልነው በሊቀ ጳጳስነቱ  ዘመን ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾምና ጾመ ሐዋርያት ከሰኞ፣ በዓለ ደብረ ዘይት፣ በዓለ ሆሳዕና፣ በዓለ ትንሣኤና በዓለ ጰራቅሊጦስ ከእሑድ፣ በዓለ ርክበ ካህናትና ጾመ ድኅነት ከረቡዕ፣ በዓለ ዕርገት ከሐሙስ፣ በዓለ ስቅለት ከዓርብ ባይወጡ፣ ባይነዋወጡ ይመኝ ነበር፡፡ እነዚህ በዓላት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነበረበት ዘመን በእነዚህ ቀናት ውለዋልና፡፡

የጻድቃን ምኞት በጎ ብቻ ነው ብሎ ጠቢቡ ሰሎሞን እንደተናገረ (ምሳሌ ፲፩፥፳፫)፤ ይህም ቅዱስ ድሜጥሮስ ይህን በጎ ሐሳብ ሲመኝና ሲያስብ ለመንፈስ ቅዱስ የተመኙትን መግለጽ ልማድ ነውና  የታዘዘ መልአክ ወደ እርሱ መጥቶ ነገር በምኞት ይገኛልን? ሱባኤ ገብተህ አግኘው ብሎ ከሌሊቱ ፳፫ (23) ሱባኤ ከቀኑ ሰባት ሱባኤ ግባ” ብሎታል፤ ስለምን “ሌሊቱን አብዝቶ ቀኑን ለምን አሳነሰው” ቢሉ ቀን የታመመ ሲጠይቅ፣ የታሰረ ሲጎበኝ፣ ወንጌል ሲያስተምር ስለሚውል ቀኑን አሳጥሮ ሌሊቱን አስረዝሞታል፡፡ አያይዞም “የሌሊቱንም የቀኑንም ሱባኤ በሰባት እያበዛህ ከ፴ (ሠላሳ) ከበለጠ በ፴ ግደፈው” ብሎታል። እንደሚታወቀው አንድ ሱባኤ ማለት ሰባት ቀናት ናቸው፡፡ ሰባት ጊዜ ሃያ ሦስት መቶ ስድሳ አንድ ይሆናል፡፡ መቶ ስድሳ አንድን በሠላሳ ስንገድፈው/ስናካፍለው/ አምስት ዐውደ ወርኅ ሆኖ ዐሥራ አንድ ይቀራል፡፡ ይህ አበቅቴ ይሁንልህ ብሎታል።

የቀኑን ሰባት ሱባኤ በሰባት ስናባዛው ዐርባ ዘጠኝ ይሆናል፡፡ በሠላሳ ስንገድፈው /ስናካፍለው/ አንድ ጊዜ ደርሶ ዐሥራ ዘጠኝ ይተርፋል፤ ይህንን “መጥቅዕ” ይሁንልህ ብሎታል። በዚህ እየቀመረ በዓላትንና አጽዋማትን አውጥቷል።

የእግዚአብሔር ድንቅ ጥበብ የተገለጠለት ይህ ቅዱስ ሰው ድሜጥሮስ የስሙ ትርጓሜ “መስታወት” ማለት ነው። መስተወት የራቀውን አቅርቦ የረቀቀውን አጉልቶ እንደሚያሳይ እርሱም በባሕረ ሐሳብ ድርሰቱ የራቀውን አቅርቦ የረቀቀውን አጉልቶ ያሳያልና ነው፡፡ አንድም “ፀሐይ” ማለት ነው፡፡ ፀሐይ ጨለማን አጥፍቶ ብርሃን እንደሚሰጥ እርሱም የደነቆረውን ጨለማውን አእምሮ በብርሃን እውቀት ያጠፋዋልና።

ትውልደ ነገዱ ከእስክንድርያ የሆነው ይህ ቅዱስ ሰው አባቱ ደማስቆ ወይም እንድራኒቆስ አጎቱ ደግሞ አርማስቆስ ወይም አስተራኒቆስ ይባላሉ። ሁለቱም በረኃብ ምክንያት ወደ ሞአብ ሀገር ተሰደው ሲኖሩ የልዕልተ ወይን አባት አርማስቆ ሚጠት(መመለስ) ሳይደረግ ዕለተ ሞቱ በደረሰ ጊዜ የልጁን የልዕልተ ወይንን ነገር ከአሕዛብ እንዳያጋባት በመልካም ሥነ ምግባር እንዲያሳድጋት አደራ ሰጥቶት ሞተ። ልዕልተ ወይንም አባቷ ከሞተ በኋላ ከአጎቷ ቤት ከድሜጥሮስ ጋራ በአንድ ላይ አፈር ፈጭተው ውኃ ተራጭተው ዘንባባ ቀጥፈው አደጉ። ሁለቱም ለአካለ መጠን በደረሱ ጊዜ የነበሩበት ቦታ አሕዛብ የበዙበት ምእመናን ያነሱበት ስለነበር ለማን እናጋባቸው ብለው ካወጡ ካወረዱ በኋላ ለአሕዛብ አጋብተናቸው ሕንጻ ሃይማኖት ከሚፈርስ እርስ በእርሳቸው አጋብተናቸው ሕንጻ ሥጋ ቢፈርስ ይሻላል ብለው እርስ በእርሳቸው አጋብተዋቸዋል። ጻድቃን ሳይቀጣጠሩ ይገናኛሉ፤ እንደሚባለው ሁለቱም ፈቃዳቸው አልነበረምና ትዳሩን ካፈረሱ ለሌላ እንዳይድሯቸው አብረው ለመኖር ተስማምተው በአንድ አልጋ ተኝተው፣ አንድ መጋረጃ ጥለው፣ አንድ አንሶላ ለብሰው፣ ወንዶችና ሴቶች በሚተዋወቁበት ግብር ሳይተዋወቁ ፵፰/48/ ዓመት ኑረዋል።

በዚህ ግብርም ሲኖር የሕዝቡ ኃጢአት ተገልጾ እየታየው ሊቆርቡ ሲመጡ “አንተ በቅተሃል ቊረብ፤ አንተ አልበቃህም ቆይ” ባላቸው ጊዜ  በዚህም “በንጹሑ በማርቆስ ወንበር ሚስቱን ይዞ እያደረ ሲሾም ዝም ብንለው ደግሞ እንዲህ ይለን ጀመር” ብለው አምተውታል፡፡

በዚህ ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተገልጾ “ኢትፍቅድ አድኅኖ ርእከ አላ ክሥት ሎሙ ክብረከ ዘሀሎ ማዕከሌከ ወማዕከለ ብሲትከ ከመ ኢይትሀጐሉ ሕዝብ በእንቲኣከ። ሕዝቡ አንተን እያሙ እንዳይጎዱ በአንተና በሚስትህ መካከል ያለውን ግለጽላቸው” ብሎታል። እርሱም “የእግዚአብሔር ፈቃድ ከሆነማ ብሎ ሕዝቡን  እንጨት እንዲያመጡ አዘዛቸው። ያን አስደምሮ በእሳት አቃጥሎ ቅዳሴ ገባ፤ ቅዳሴውን ሲጨርስ ልብሰ ተክኖውን እንደለበሰ ማዕጠንተ ወርቁን ይዞ በእሳቱ መካከል ያጥን ነበር። አንድም “ከደመራው ላይ ቁሞ በእሳት አቃጥሉት” አላቸው። “በምን ምክንያት እንሽረዋለን ስንል በፈቃዱ ገብቶ ሊሞትልን ነው” አሉት። እርሱ ግን ምንም ሳይሆነው በመካከሉ እየተመላለሰ ያጥንና ይጸልይ ጀመር። ሚስቱንም ከምቅዋመ አንስት ከመካነ ደናግል ነበረችና አስጠርቶ ስትመጣ “ስፍሒ አጽፈኪ፤ ልብስሽን ዘርጊ” ብሎ ከፍሕሙ በእጁ እያፈሰ ከአጽፋ ላይ አደረገላትና አስታቅፎ “እየዞርሽ ተናገሪ” አላት፡፡ እርሷም ሦስት ጊዜ እየዞረች ፵፰ /48/ ዓመት ሲኖሩ በልማደ መርዓት ወመርዒዊ እንደማይተዋወቁ ገለጸችላቸው። ሕዝቡም ከጫማው ሥር ወድቀው “ኅድግ ለነ አበሳነ፤ አባታችን በድለናል ይቅር በለን” አሉት። እርሱም “ይኅድግ ይፍታሕ፤ እግዚአብሔር ይፍታ” ብሎ ናዟቸዋል፤ ኑዛዜም የተጀመረ በዚህ ጊዜ ነው።

የአባታችን ቅዱስ ድሜጥሮስ ጸሎት፣ ምልጃ እና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

 

 

 

 

 

 

 

መጽሔተ ተልእኮ ዘማኅበረ ቅዱሳን

መጽሔተ ተልእኮ ዘማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃና መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ሕዝብ ግንኙነትና ትብብር አገልግሎት ማስተባበሪያ የተዘጋጀ ነው፡፡ ከታች ያለውን ሊንክ በመጫን መጽሔቱን ያንብቡ!

ጌታችን ፈዋሽ ውኃን አፈለቀ!

ሰኔ ስምንት ቀን አምላክን የወለደች በሁለት ወገን ድንግል የሆነች የእመቤታችን ማርያም የታወቀችው በውኃ ምንጭ ዘንድ ያለች የቤተ ክርስቲያንዋ ቅዳሴ ነው:: እርሱም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእርሷ ጋር ወደ ግብጽ አገር ተሰዶ ሲመለስ ያፈለቀው የተባረከ መታጠቢያ ነው::

ቃና ዘገሊላ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንደ ሙሽራ አጊጣ፣ ለበጉ ሰርግ ያለ እድፍና ያለ ነውር ውብ ሆና ተዘጋጅታ በምትቀርብበት በዚያ ሰማያዊ ሰርግ ለመገኘትና ወደ በጉ ሰርግ ራት ገብተን፣ ካጌጡ ቅዱሳን ጋር ለመቀመጥና ለመብላት የበቃን ያድርገን፡፡

መልካም እረኛ!

“እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ወደ በጎች በረት በበሩ የማይገባ በሌላ መንገድ ግን የሚወጣ እርሱ ሌባ ወንበዴም ነው፤ በበሩ የሚገባ ግን የበጎች እረኛ ነው። ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፤ በጎቹም ድምፁን ይሰሙታል፥ የራሱንም በጎች በየስማቸው ጠርቶ ይወስዳቸዋል። የራሱንም ሁሉ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸው ይሄዳል፥ በጎቹም ድምፁን ያውቃሉና ይከተሉታል፤ ከሌላው ግን ይሸሻሉ እንጂ አይከተሉትም፥ የሌሎችን ድምፅ አያውቁምና።”

ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ

የአባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያት ተጋድሎ በጽኑ መሠረት ላይ በመገንባቱ የመከራ ዝናብ ቢዘንብ፣ የሥቃይ ጎርፍ ቢጎርፍ፣ የችግር ነፋስ ቢነፍስ አይወድቅም፡፡ (ማቴ.፯፥፳፭) ይህም የሆነው እነርሱን በመንፈሳዊ ሕይወት የተተከለ፣ በተጋድሎ ያሳደገ፣ ገቢረ ተአምራት ወመንክራት በማድረግ እንዲያብቡ ያደረገና ለፍሬ ክብር ያበቃ የክብር ባለቤት አምላካችንና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመሆኑ ነው፡፡

“በውኑ የምታነበውን ታስተውለዋለህን ?” (ሐዋ.፰፥፴)

ብዙዎች ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ወጥተው የቀሩት የመጽሐፍ ቅዱስን ንባብ እንዲሁ በፈቃዳቸው እና በግል ምልከታቸው ለመተርጎም በሚያረጉት ሙከራ ነው። ቤተ ክርስቲያን ግን እንደ ሠለስቱ ምዕት፣ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ቅዱስ ጎርጎርዮስ፣ ቅዱስ ቄርሎስ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን የመሳሰሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የጻፏቸውን ድርሳናትና ትርጓሜያት ለልጆቿ በማስተማር ከግል አረዳድ ወጥተን የተነገረበትን ትክክለኛ ዐውድና ምሥጢር ጠብቀን እንድንረዳ ታስተምረናለች፡፡

የአምላክ እናት መገለጥ!

እንኳን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም ‹‹በዓለ ደብረ ምጥማቅ›› አደረሳችሁ!

አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ በስሟ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ላይ በብርሃን መርከብ ተቀምጣ ፊቷ በግልጥ ስለ መታየቱ የክርስቲያን ወገኖች ሁላችንም ታላቅ በዓልን እናደርጋለን።