ቅድስት አፎምያና ባሕራን
ውድ የእግዚአብሔር ልጆች እንዴት አላችሁልን? በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዐዋጅ ታውጀው ከሚጾሙ አጽዋማት አንዱ የሆነው ጾመ ሐዋርያት የሚጾምበት ወቅት ላይ ነንና ይህን ጾም እንዴት እያሳለፋችሁት ነው? አባቶቻችንን ቅዱሳን ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስ ጸጋን ከተቀበሉ በኋላ ወደ አገልግሎት ከመሄዳቸው በፊት ጾምን ጾመዋል፤ ይህን ጾም ምእመናን በየዓመቱ በዓለ ኀምሳ ከተከበረ ማግስት ጀምሮ እስከ ሐምሌ አምስት ቀን ድረስ እንጾመዋለን፤ ልጆች! እንግዲህ እኛም እንደ አቅማችን ይህንን ጾም መጾም ይገባናል፤ በዘመናዊ ትምህርታችሁም ከፈተና በፊት በርትታችሁ በማጥናት ፈተናውን በደንብ መሥራት ይገባችኋል ፤ መልካም! ለዛሬ ስለ ቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት እንማራለን፡፡
ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ቅዱሳን መላእክት ከእግዚአብሔር ተልከው እኛን የሚጠብቁን ናቸው፤ መልካም ስንሠራ ችግር በገጠመን ጊዜ በጸሎት ስንማጸናቸው ፈጥነው በመምጣት ከዚያ መከራ ያወጡናል፤ ከእግዚአብሔር አማልደው ምሕረትን ያሰጡናል፡፡ ከቅዱሳን መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ሚካኤል ከመከራ ካዳናቸው መካከል ሁለቱን ታሪክ አንሥተን ለዛሬ እንማራለን፡፡