ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር
ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁ? ክረምቱንስ እንዴት እያሳለፋችሁት ነው? የዚህን ዓመት የትምህርት ጊዜ ጨርሳችሁ ዕረፍት ላይ ናችሁና በዚህ ወቅት ከቤት ስትወጡ፣ ከቦታ ቦታ ስትንቀሳቀሱ በጥንቃቄ መሆን አለበት፡፡ ከበድ ያለ ዝናብ ሲጥል ድንገት ጉዳት ሊያደርስ ስለሚችል ሁሉን በጥንቃቄ ልናደርገው ይገባል፤ ደግሞም ይህንን ወቅት ቴሌቪዥን ብቻ በማየት ወይም በጨዋታ ማሳለፍ የለብንም፤ ለቀጣዩ የትምህርት ዘመን ሊረዱን የሚችሉ መጻሕፍትን ልናነብ ይገባል እንጂ፡፡
ሌላው ደግሞ በአቅራቢያችሁ ባለው ቤተ ክርስቲያን በመሄድ የአብነትና የሥነ ምግባር ትምህርት መማር አለባችሁ፤ ልጆች! ባሳለፍነው የትምህርት ዘመን ጥሩ ውጤት ያላመጣን ካለን በሚቀጥለው በርትቶ በመማርና በማጥናት በመጪው ዓመት የፈተና ወቅት ጥሩ ውጤት ማምጣት ያስፈልጋል፡፡ መልካም!
ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ባለፈው ስለ መልካም ምግባራት ተምረናል፤ እንዲሁም ከመልካም ምግባራት (ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር) መካከል ስለ ፍቅርና፣ ስለ መታመን ተምረን ነበር፤ ለዛሬ ደግሞ ስለ መታዘዝና ይቅርታ እንማራለን፡፡