ሥዕለ አድኅኖ

 ክፍል ሁለት

ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ 

ኀዳር ፩፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? በዘመናዊ ትምህርታችሁስ እየበረታችሁ ነው? ትምህርት ከተጀመረ ሁለት ወርን አስቆጥረናል፡፡ ምን ያህል ዕውቀትን ገበያችሁ? ጊዜ አለን ብላችሁ እንዳትዘናጉ የተማራችሁትን ወዲያው በመከለስ አጥኑ፤ ያልገባችሁን ደግሞ መምህራንን ጠይቁ፤ በሰንበት እሑድ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መማርና ማገልገልን እንዳትረሱ፡፡ መልካም! ባለፈው ትምህርታችን ስለ ቅዱሳት ሥዕላት በተማርነው ትምህርት ቅዱስ ማለት ምን ማለት እንደሆነ፣ ሥዕል ማለት ምን ማለት እንደሆነና ለምን ቅዱሳት ሥዕላት እንደሚሣሉ በመጠኑ ተመልክተናል፡፡ ለዛሬ ደግሞ ቀጣዩን ክፍል  “ሥዕለ አድኅኖ” በሚል ርእስ ስለ ቅዱሳት ሥዕላት አሣሣል ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! አድኅኖ ማለት “ማዳን፣ መታደግ፣ መቤዠት፣ ነጻ ማውጣት” ማለት ነው፡፡ (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ መዝገበ ቃላት ገጽ ፫፻፵፬)፤ “ሥዕል ማለት ምን ማለት ነው” የሚለውን ባለፈው ትምህርታችን ነግረናችኋል፤ ሥዕለ አድኅኖ የሚለው ስያሜ የሚሰጠው ለቅዱሳት ሥዕላት ነው፡፡ ሥዕለ አድኅኖ ስንል የሚታደጉ፣ ከክፉ የሚጠብቁ ቅዱሳት ሥዕላት ማለት ነው፡፡

የሥዕለ አድኅኖ አሣሣል

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! የሥዕለ አድኅኖ የራሳቸው የሆነ አሣሣል አላቸው፤ ዝም ብሎ በዘፈቀደ አይሳሉም፤ ለሥዕለ አድኅኖ የምንጠቀምባቸው ቀለማት እያንዳንዳቸው የራሳቸው የሆነ ትርጕም (ምሥጢር) ምሳሌ ስላላቸው ያንን ምሥጢር ጠብቀው መሳል አለባቸው፡፡ የራሳቸው የሆነ ልዩ የሚያደርጋቸው መለያ ባሕርያት አሏቸው፡፡ የቀለም አቀባቡ፣ የሚሣሉበት ቦታ፣ ለሥዕላቱ የሚሰጠው ክብር፣ ከሌሎች ሥዕላት  የሥዕለ አድኅኖ በሚሣሉበት ጊዜ ዋና ትኩረት ለሥዕሉ ባለቤት መንፈሳዊ ማንነት ላይ ያኩራል፡፡ ሥዕላቱ ሲሣሉ ባለቤቱ እንደዚህ ይመስላል ለማለት አይደለም፡፡ ሥዕላቸው ሲሣል ከገድላቸው መካከል፣ ካደረጉት ተአምራት መካከል ዋና የሆነውን ጎልቶ የሚታወቀውን ሥራቸውን የሚያንጸባርቅ (የሚያስተምር፣ የሚገልጥ)  ነው፡፡

 ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለምሳሌ የቅዱሳን አባቶቻችንን ሥዕል ብንመለከት የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ሥዕል ለሃያ አንድ ዓመት ቆመው ሲጸልዩ አንድ እግራቸው ከመቆማቸው ብዛት ብትሰበር (ብትቆረጥ) እግዚአብሔር የጸጋን ክንፍ እንደሰጣቸው በአንድ እግራቸው ቆመው ሲጸልዩ ይሣላል፡፡ የተቆረጠው እግራቸው በክብር አርፎ፣ ጦር ከጎናቸው ተክለው በተመስጦ ሲጸልዩ ተሥሎ ስንመለከት ተጋድሏቸውን፣ የጸሎት ሕይወታቸውን፣ በሥዕሉ ውስጥ እናስተውላለን፡፡

ባለፈው ትምህርታችን ሥዕለ አድኅኖ የሚሣልበት ምክንያት ለምንድን ነው የሚለውን ስንማር ለመታሰቢያ እንዲሁም ለመማሪያ እንዲሆን የሚለውን ተመልክተን ነበር፤ “የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው።” (መዝሙረ ዳዊት ፻፲፪፥፮) በዚህም መሠረት አሁን ለምሳሌ በገለጽነው የጻድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሥዕል በዚህ መልኩ መሳሉ ብዙ ነገሮችን እናገኝበታለን፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ሌላ ምሳሌ ደግሞ እንመለከት፤ የቅዱሳን መላእክት ሥዕል ሲሣል በድርሳናት፣ በስንክሳር እንዲሁም በተለያዩ ቅዱሳት መጻሕፍት ላይ መላእክቱ ከእግዚአብሔር ተልከው የሰው ልጆችን ለመራዳት ሲመጡ በወቅቱ በተገለጹበት አምሳል ይሣላሉ፤ እንደ አብነት ብንወስድ ቅዱስ ገብርኤል ሦስቱ ወጣቶች አናንያ፣ አዛርያና ሚሳኤል “ለጣዖት አንሰግድም፤ እግዚአብሔርን አንክድም” ብለው በሃይማኖታቸው በመጽናታቸው ናቡከደነጾር የተባለ ንጉሥ እሳት አስነድዶ ከዚያ ሲያስጨምራቸው ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ መጣና እሳት ውስጥ አብሯቸው ሆነ፤ ከሚነደው እሳት አዳናቸው፡፡ (ት.ዳን ፫፥፩-፴)

ታዲያ ይህንን ታሪክ በሥዕል ለማስተማር በሚነድ እሳት ውስጥ ሦስቱ ወጣቶችና ቅዱስ ገብርኤል ይሣላሉ፡፡ ሌሎችንም የቅዱሳን መላእክት ሥዕለ አድኅኖ የሚሣለው በዚሁ መልክ ነው፡፡ (በወቅቱ በተገለጹት አኳኻን)፡፡ የቅዱሳን መላእክትን ሥዕለ አድኅኖ ስንመለከት መስቀል፣ ሰይፍ፣ ይዘው ይሣላሉ፡፡ መስቀል መያዛቸው ለምሕረት፣ ሰዎችን ለማዳን መላካቸውን ለመግለጽ፣ ሰይፍ መያዛቸው ደግሞ ክፉ ሰዎችን ለመቅጣት መላካቸውን ለመግለጽ ነው፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  የሥዕለ አድኅኖ የአሣሣል ዘዴ፣ የሚሣሉበት ጥበብ ከሌሎች አገራት የአሣሣል ትውፊት ይለያል፡፡ ሥዕለ አድኅኖዎች ሲሳሉ የፊት ቅርጻቸው ጎልቶ ይሣላል፡፡ በራሳቸው ላይም የብርሃን አክሊል ይሣላል፡፡ ጎላ (ተለቅ) ተደርጎ መሣሉ የጎላች የተረዳች ሃይማኖት (ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ) ያላቸው ጠብቀውም የኖሩ ዓይናቸው ጎላ ተደርጎ ይሣላል፡፡ ዓይናቸው የሚመጣውን ያለፈውንም ዓለም በትንቢት መነጽርነት ይመለከታሉና የጎላ ዓይን ሁሉን የሚመለከት ንጹሕ ዓይን እንዳላቸው ለማሳየት ዓይናቸው ጎልቶ ይሣላል፡፡ በራሳቸው ዙሪያ ደግሞ ክብ ቅርጽ ያለው ብርሃን ያለው ተደርጎ ይሣላል፤ ይህም የሚገልጸው ክብራቸውንና ንጽሕናቸውን ነው፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለዛሬ ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል ምንን ምክንያት (መሠረት) አድርጎ እንደሆነና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሥዕለ አድኅኖ እንዴት እንደሚሳል ምሳሌነቱን በመጠኑ ተመልክተናል፤ በቀጣይ ክፍል ሥዕለ አድኅኖ ሲሣል የምንጠቀማቸው ቀለማት (ከለር) ምን ዓይነት መሆን እንዳበትና ምክንያቱን እንዲሁም በሥዕለ አድኅኖ ከተደረጉ ተአምራት የተወሰኑትን ለአብነት እንመለከታለን፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ በትምህርታችሁ በርትታችሁ ተማሩ፤ ለወላጅ መታዘዝን፣ ለሰዎች መልካም ማድረግን እንዳትረሱ፤ በሰንበት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መንፈሳዊ ትምህርትንም ተማሩ፡፡ ይቆየን ቸር ይግጠመን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ወለወላዲቱ ድንግል

ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

 

 

 

 

 

 

ቅዱሳት ሥዕላት

ክፍል አንድ
ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ
ጥቅምት ፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? በአዲሱ ዓመት የመጀመሪያ ትምህርታችን የሆነውን በፈቃደ እግዚአብሔር ጀምረናል፤ ባሳለፍነው ዓመት በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ስንማር ቆይተን ከዚያም ክለሳ አድርገን ጥያቄና መልስ ማዘጋጀታችን ይታወሳል፡፡ እናንተም ለቀረበላችሁ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ተሳትፋችኋል፤ ጥሩ ውጤት ላስመዘገቡ የማበረታቻ ስጦታንም አበርክተንላቸዋል፡፡ (ሰጥተናቸዋል)፤ እንግዲህ በዚህም ዓመት የምናቀርብላችሁን ትምህርት በደንብ ደግሞ መከታተል እንዳለባችሁ ማሳሰብ እንወዳለን፡፡

መርሳት የሌለባችሁ ሌላው ነገር በዘመናዊ ትምህርታችሁ ከአሁኑ ያልገባችሁን በመጠየቅ፣ የቤት ሥራን በመሥራት፣ በማጥናት ጎበዞችና አስተዋይ ልጆች መሆን እንዳለባችሁ ነው!

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ወላጆቻችን ከእኛ በጣም ብዙ ነገር ይጠብቃሉ፤ ጥሩ ውጤት እንድናመጣ፣ ወደፊት ትልቅ ደረጃ እንድንደርስም ይመኛሉ፤ ስለዚህም እኛ ስንፍናን አርቀን፣ ጨዋታን ቀንሰን፣ በርትተን በመማርና በማጥናት ጎበዝ ልጆች መሆን ይገባናል! ወላጆቻችንን እኛን ለማስተማር ብዙ ነገርን ያደርጋሉ፤ ታዲያ እኛ ጎበዞች በመሆን ደስተኞች ልናደርጋቸው ይገባል፡፡ መልካም! በአዲሱ ዓመት በመጀመሪያው ትምህርታችን ስለ ቅዱሳት ሥዕላት እንማራለን፡፡

ወላጆች ከእኛ ጋር ትምህርት ቤት አይሄዱም፤ ከእኛ ክፍል ገብተው አብረውን አይማሩም፤ ግን ልጆቻችን ትምህርት ቤት ሄደው ተምረው ይመጣሉ ብለው አምነው ይልኩናል! አያችሁ እኛ ትምህርት ቤት ገብተን ተምረን በአግባቡ ወደ ቤት በመመለስ መታመናችንን መግለጥ (ማሳየት) ይገባናል፡፡

ቅዱሳት ሥዕላት

‹‹ሥዕል›› ማለት “መልክ፣ የመልክ ጥላ፣ ንድፍ፣ አምሳል፣ ንድፍ በውኃ፣ በመጽሔት፣ በጥልፍ፣ በስፌት ወይም በቀለም በወረቀት ገዝፎ ተጽፎ፣ ከዕብን፣ ከዕፅ፣ ከማዕድን ታንጦ፣ ተቀርጦ፣ ተሸልሞ፣ አጊጦ የሚታይ የሚዳሰስ ነገር” ነው፡፡›› (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ መዝገበ ቃላት)
ቅዱሳት የሚለው ቃል ደግሞ «ቀደሰ» ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጒሙም “ለየ፣ አከበረ፣ መረጠ” ማለት ነው። ውድ

የእግዚአብሔር ልጆች ቅዱሳት ሥዕላት ለእግዚአብሔር የተለዩ፣ የተቀደሱ፣ ልዩ፣ ምርጥ፣ ንጹሕ እና ጽሩይ የሆኑ የቤተ መቅደሱ መገልገያ ንዋያተ ቅድሳት በመሆናቸው «ቅዱሳት» ተብለው ይጠራሉ። እንዲሁም ደግሞ ቅዱሳት ሥዕላት የቅዱሳንን ታሪክ እና ማንነት በጊዜው ላልነበርን በመንፈስ ዓይን እንድናይ ስለሚያደርጉን፣ አንድም ሥጋዊውን ዓለም ከሚያንጸባርቁ ዓለማውያን ሥዕላት ፈጽመው የተለዩ በመሆናቸው፣ አንድም የቅዱሳን ቅድስና ሥዕላቱን ቅዱስ ስላሰኛቸው፣ አንድም በሥዕላቱ አድሮ እግዚአብሔር ስለሚፈጽመው ገቢረ ተአምራት የተነሣ ሥዕላቱ «ቅዱሳት ሥዕላት» ተብለው ይጠራሉ።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት ሥዕላት ተብለው የሚጠሩት ሐዋርያዊ ትውፊትንና ቀኖናን ጠብቀው የሚሣሉ የቅዱስ እግዚአብሔር፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ የቅዱሳን መላእክት፣ የቅዱሳን ነቢያት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት እና የሌሎች ቅዱሳን ጻድቃን ማንነት፣ ሕይወትና ታሪክ የሚያሳዩ እና የሚወክሉ ሥዕሎች ናቸው፡፡

የቅዱሳንን ሥዕል መሳል ለምን አስፈለገ?

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ቅዱሳን ሥዕላትን በመሳል ለአገልግሎት እንጠቀም ዘንድ ያዘዘን እራሱ የሰማይና ምድር ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ የቃል ኪዳኑን ማደሪያ ታቦት እንዴት እንደሚሠራ ሲነግረው እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ብሎ እንዳዘዘው እናነባለን፤ “ከሥርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን፥ ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርገህ በአንድ ላይ ትሠራዋለህ።” (ዘፀ.፳፭፥፲፱) ይህንንም ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሙሴ መፈጸሙን ሲገልጥልን “ከስርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን፥ ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርጎ በአንድ ላይ ሠራቸው። ክንፎቻቸውን ወደላይ የዘረጉ ሆኑ” በማለት መስክሮታል። (ዘፀ. ፴፯፥፰-፱)

የቅዱሳንን ሥዕል መሳል ያስፈለገው የቅዱሳን መታሰቢያ /ማዘከርያ ስለሆነ፦ እግዚአብሔር አምላካችን ቅዱሳንን ስለ ቅድስናቸው እንዲሁም ስለ እርሱ ብለው ለፈፀሙት ተጋድሎ እንድናስባቸውና እንድንዘክራቸው ትእዛዝ እንዲህ ሲል አስተላልፎልና፤ “በቤቴና በቅጥሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያ ስም እሰጣቸዋለሁ፣ የማይጠፋ የዘለዓለም ስም እሰጣቸዋለሁ፡፡” (ኢሳ.፶፮፥፭)።

በሌላም በኩል (በመጽሐፈ ምሳሌ ፲፥፯) “የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው።” (መዝሙረ ዳዊት ፻፲፪፥፮) “የጻድቅ መታሰቢያ ለዘለዓለም ይኖራል” ተብሎ እንደተመሠከረላቸው በረከታቸውን ለማግኘት ለመታሰቢያቸው መለያቸውን ቅዱሳት ሥዕላት እንጠቀማለን።

ሌላው ደግሞ ከእነርሱ በረከት አልፈን ቅዱሳት ሥዕላት በተሳሉበት በቅድስና ስፍራው እግዚአብሔር ራሱንም ስለምናገኝበት ነው፤ ለሊቀ ነቢያት ሙሴ “በዚያም ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል በሥርየት መክደኛው ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ” ብሎታልና። (ዘፀ.፳፭፥፳፪)

ጠቢቡ ሰሎሞን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ባነፀ (በሠራ) ጊዜ ቅዱሳት ሥዕላትን ሠርቶ ነበር፤ “በቅድስተ ቅዱሳኑም ውስጥ ቁመታቸው ዐሥር ክንድ የሆነ ከወይራ እንጨት ሁለት ኪሩቤል ሠራ፤ ኪሩቤልንም በወርቅ ለበጣቸው፤ በቤቱም ግንብ ሁሉ ዙሪያ በውስጥና በውጭ የኪሩቤልና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸ፤ ሁለቱንም ደጆች ከወይራ እንጨት ሠራ፤ የኪሩቤልንና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸባቸው፥ በወርቅም ለበጣቸው፤ ኪሩቤልንና የዘንባባውን ዛፍ በወርቅ ለበጣቸው፤ የኪሩቤልንና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸባቸው፤ በተቀረጸውም ሥራ ላይ በወርቅ ለበጣቸው” ተብሎ ተጽፏል። (፩ኛ ነገ ፮ ፥፳፫-፴፭)።

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! በዘመነ ሐዋርያት ደግሞ ቅዱስ ሉቃስና ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ቅዱሳት ሥዕላትን ይሥሉ ነበር። ነባቢ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ የተመለከታትን የቃል ኪዳኑ ታቦት ነው፡፡ (ራእይ ፲፩፥፲፱)

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለዛሬ ስለ ቅዱሳት ሥዕላት የቃሉን ፍቺ እና ቅዱሳት ሥዕላት ለምን እንደሚሳሉ በመጠኑ ተመልክተናል፤ በቀጣይ ስለ ቅዱሳት ሥዕላት ጥቅምና አሳሳል እንመለከታለን፡፡ (ምንጭ ኦርዶክሳዊ ቅዱሳት ሥዕላት አሳሳል)
ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ በትምህርታችሁ በርትታችሁ ተማሩ! ለወላጅ መታዘዝን፣ ለሰዎች መልካም ማድረግን እንዳትረሱ፤ በሰንበት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መንፈሳዊ ትምህርትንም ተማሩ፡፡ ቸር ይግጠመን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

የቱን ታስታውሳላችሁ?

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? በየዓመቱ በጉጉት የምጠብቃት ጾመ ፍልሰታ እንዴት አለፈ? እንዴት አቅማችን በመጾም፣ በመጸለይ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከቤዛዊት ዓለም በረከትን ተቀብለን እንዳለፍንበት ተስፋችን እሙን ነው፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ከጾመ ፍልሰታ በፊት “የቱን ታስታውሳላችሁ?” በሚል ርእስ ስንማራቸው ከነበሩ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር መካከል የተወሰነ ጥያቄዎችን ጠይቀናችሁ እናንተም ምላሹን ልካችሁልን ነበር፤ ለጥያቄዎቹ ተገቢውን ምላሽ ለሚሰጡም እንደተለመደው ሽልማቶችን እንደምናዘጋጅ ነግረናችሁ ነበር፡፡ የሽልማት መርሐ ግብሩን በተለየ መርሐ ግብር እናዘጋጃለን፡፡

የቱን ታስታውሳላችሁ?

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? እንኳን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤና ዕርገት መታሰቢያ ለሆነው ጾመ ፍልሰታ አደረሳችሁ፡፡ ልጆች! በየዓመቱ በጉጉት የምንጠብቃት ጾመ ፍልሰታን እንደ አቅማችን በመጾምና በመጸለይ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከቤዛዊተ ዓለም በረከትን መቀበል ይገባናል፤ ልጆች! በጾመ ፍልሰታ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ፣ ትምህርት በመማር፣ በማስቀደስ፣ መልካም ምግባራትን በመፈጸም መሳተፍ አለብን፡፡

ልጆች! በዛሬ “የቱን ታስታውሳላችሁ?” መርሐ ግብራችን ባሳለፍነው ዓመት ስንማራቸው ከነበሩ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባራት መካከል የተወሰነ ጥያቄን አዘጋጅተንላችኋል፡፡ ከዚህ ቀደም የአስተማርናችሁን ትምህርት በደንብ ከልሷቸው፤ ከዚያም ለጥያቄዎቹ ተገቢውን ምላሽ በድረ ገጽ አድራሻችን “website.amharic@eotcmk.org” እና “https://t.me/Hiwot122716” ትልኩልናላችሁ! እንደተለመደው ጥሩ ውጤት ለሚያመጡ ልጆች ሽማቶችን አዘጋጅተናል፡፡

ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁ? ክረምቱንስ እንዴት እያሳለፋችሁት ነው? የዚህን ዓመት የትምህርት ጊዜ ጨርሳችሁ ዕረፍት ላይ ናችሁና በዚህ ወቅት ከቤት ስትወጡ፣ ከቦታ ቦታ ስትንቀሳቀሱ በጥንቃቄ መሆን አለበት፡፡ ከበድ ያለ ዝናብ ሲጥል ድንገት ጉዳት ሊያደርስ ስለሚችል ሁሉን በጥንቃቄ ልናደርገው ይገባል፤ ደግሞም ይህንን ወቅት ቴሌቪዥን ብቻ በማየት ወይም በጨዋታ ማሳለፍ የለብንም፤ ለቀጣዩ የትምህርት ዘመን ሊረዱን የሚችሉ መጻሕፍትን ልናነብ ይገባል እንጂ፡፡

ሌላው ደግሞ በአቅራቢያችሁ ባለው ቤተ ክርስቲያን በመሄድ የአብነትና የሥነ ምግባር ትምህርት መማር አለባችሁ፤ ልጆች! ባሳለፍነው የትምህርት ዘመን ጥሩ ውጤት ያላመጣን ካለን በሚቀጥለው በርትቶ በመማርና በማጥናት በመጪው ዓመት የፈተና ወቅት ጥሩ ውጤት ማምጣት ያስፈልጋል፡፡ መልካም!

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ባለፈው ስለ መልካም ምግባራት ተምረናል፤ እንዲሁም ከመልካም ምግባራት (ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር) መካከል ስለ ፍቅርና፣ ስለ መታመን ተምረን ነበር፤ ለዛሬ ደግሞ ስለ መታዘዝና ይቅርታ እንማራለን፡፡

ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁ? የባለፈው የትምህርት ቆይታችሁ ውጤታችሁ እንዴት ነው? መቼም ጠንክራችሁ ስትማሩ ስለነበር በጥሩ ውጤት እንዳለፋችሁ ተስፋ እናደርጋለን! ወርኃ ክረምቱንስ እንዴት ተቀበላችሁት? እንዴትስ ልታሳልፉት አቀዳችሁ! ይህንን ከወዲሁ ማሰብ አለባችሁ! የዕረፍት ጊዜ ነው ብላችሁ በጨዋታ ማሳለፍ የለባችሁም፡፡ በአቅራቢያችሁ ባለው ቤተ ክርስቲያን በመሄድ በሰ/ት/ቤት በመግባት በአብነት ትምህርቱንና የሥነ ምግባር  ትምህርትን መማር አለባችሁ፤ ውድ ልጆች! ባሳለፍነው የትምህርት ዘመን ጥሩ ውጤት ያላመጣን ካለን በሚቀጥለው በርትቶ መማርና፣ ለማጥናት በመጪው ክረምት ወቅት ማጥናት ያስፈልጋል፡፡ 

ውድ ልጆች! ለዛሬ ያዘጋጀልናችሁ ባለፉት ጊዜያት ስንማራቸው የነበሩትን ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባራትን ክለሳ ነው፤ አሁን የተወሰነውን በቀጣይ ደግሞ ቀሪውን እንማራለን! ታዲያ ጥያቄና መልስ  ለመለሱ ተማሪዎች እንደተለመደው ሽልማት ስለምናዘጋጅ በደንብ አንብቡና ተዘጋጁ፤ መልካም!

ቅድስት አፎምያና ባሕራን

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች እንዴት አላችሁልን? በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዐዋጅ ታውጀው ከሚጾሙ አጽዋማት አንዱ የሆነው ጾመ ሐዋርያት የሚጾምበት ወቅት ላይ ነንና ይህን ጾም እንዴት እያሳለፋችሁት ነው? አባቶቻችንን ቅዱሳን ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስ ጸጋን ከተቀበሉ በኋላ ወደ አገልግሎት ከመሄዳቸው በፊት ጾምን ጾመዋል፤ ይህን ጾም ምእመናን በየዓመቱ በዓለ ኀምሳ ከተከበረ ማግስት ጀምሮ እስከ ሐምሌ አምስት ቀን ድረስ እንጾመዋለን፤ ልጆች! እንግዲህ እኛም እንደ አቅማችን ይህንን ጾም መጾም ይገባናል፤ በዘመናዊ ትምህርታችሁም ከፈተና በፊት በርትታችሁ በማጥናት ፈተናውን በደንብ መሥራት ይገባችኋል ፤ መልካም! ለዛሬ ስለ ቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት እንማራለን፡፡

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ቅዱሳን መላእክት ከእግዚአብሔር ተልከው እኛን የሚጠብቁን ናቸው፤ መልካም ስንሠራ ችግር በገጠመን ጊዜ በጸሎት ስንማጸናቸው ፈጥነው በመምጣት ከዚያ መከራ ያወጡናል፤ ከእግዚአብሔር አማልደው ምሕረትን ያሰጡናል፡፡ ከቅዱሳን መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ሚካኤል ከመከራ ካዳናቸው መካከል ሁለቱን ታሪክ አንሥተን ለዛሬ እንማራለን፡፡

ምጽዋት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? እንኳን ለብርሃነ ዕርገቱ እንዲሁም ለበዓለ ኀምሳ አደረሳችሁ! ለአባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ የወረደበትን በዓለ ኀምሣ ባከበርን ማግስት ጾመ ሐዋርያት ይገባል፡፡ አባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስ ጸጋን ከተቀበሉ በኋላ ጥበብ ማስተዋሉን አግኝተው በእምነት ጸንተው የምሥራቹን ወንጌል ለማስተማር ከመሄዳቸው በፊት ጾምን ጾመዋል፡፡ ይህን ጾም ሁል ጊዜ ከበዓለ ኀምሳ ማግሥት ጀምሮ እስከ ሐምሌ አምስት ድረስ እንጾመዋለን፡፡

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዐዋጅ ከሚጾሙ ሰባቱ አጽዋማት አንዱ ይህ ጾመ ሐዋርያት ወይም በተለምዶ የሰኔ ጾም እየተባለ የሚጠራው ነው፤ እኛም በአቅማችን ይህንን ጾም ልንጾም ይገባናል፤ ከአባቶቻችንን ቅዱሳን ሐዋርያት በረከትን ለማግኘት፣ ጾሙን እንጽም፤ በዘመናዊ ትምህርታችን ትምህርት ጨርሰን የማጠቃለያ ፈተና የምንፈተንበት ወቅት ነውና በርትተን እናጥና ፤ በመጪው ክረምትም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመገኘት መንፈሳዊ ትምህርትን ለመማር ከአሁኑ እናቅድ (እንዘጋጅ) መልካም! ውድ ልጆች! ለዛሬ የምንማረው ስለ “ምጽዋት” ነው፡፡

ተስፋ መንግሥተ ሰማያት!

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? በዓለ ኀምሳን እንዴት አያሳለፋችሁ ነው? በዓለ ዕርገትም እየደረሰ ነውና በዓሉን ለማክበር መዘጋጀት ያስፈልጋል! ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከማረጉ በፊት በተለያየ ጊዜ ለቅዱሳን ሐዋርያት እየተገለጠላቸው ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ያስተምራቸው ነበር፡፡ በዚህም መሠረት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስናገለግል በሥርዓት ነው፡፡ በትምህርታችንም መበርታት እንዳለብን እንረዳለን፡፡ የፈተና ወቅት እየደረሰ በመሆኑ ከዚያ በፊት በርትተን በማጥናት ዕውቀት አግኝተን ከክፍል ወደ ቀጣይ ክፍል በጥሩ ውጤት መሸጋገር ይገባናል፤ መልካም ልጆች! ለዛሬ ስለ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት እንማራለን፡፡

‹‹ለሁሉም ጊዜ አለው›› (መክብብ ፫፥፩)

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? የትንሣኤን በዓል ወቅት (በዓለ ኀምሳን) እንዴት እያሳለፋችሁ ነው? በሰንበት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ እያስቀደሳችሁ እንደሆነ ተስፋችን እሙን ነው! የአካዳሚ (ዘመናዊ) ትምህርትስ ጠንክራችሁ እየተማራችሁ ነውን! የዓመቱ ትምህርት የሚያበቃበት ጊዜ እየደረሰ ነው! አንዳንዶች ፈተና የምትፈተኑበት ጊዜው በጣም ደርሷል፡፡ በርትታችሁ በመማር፣ በማጥናት ጥሩ ውጤት ማስመዝገብ አለባችሁ፡፡

ልጆች! ያላችሁበት ወቅት ዓለማችን ከብዙ ሥልጣኔ ደረጃ የደረሰችበት ነው። ታዲያ እናንተም ከዚህ እኩል እንድትራመዱ በርትታችሁ በመማር ችግር ፈቺ፣ መፍትሔ አምጪ መሆን አለባችሁና በርቱ! ባለፈው ትምህርታችን ስለ ሰላም ተምረን ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ ስለ “ጊዜ” እንማራለን! መልካም!