መልካም አስተዳደር ለሀገር ሰላም
የመልካምነት ሁሉ መገኛ የሆነችው፣ ሰብሳቢያችን፣ አስተማሪያችን፣ ቅድስት ስፍራ፣ የእውነተኛ ሕይወት መገኛ፣ የአምላክ ቤት መቅደሳችን በዚህ ጊዜ ተከፍታለች፡፡ ልጆቿን በስደት፣ በሞትና በኃጢአት በማጣቷ ሰላምን ማግኘት አልቻለችም፡፡ ይህን ሰላም ማግኘት የምትችለውም ልጆችዋን በቤቷ ስትሰበስብና በመልካም አስተዳደር ማኖር ስትችል መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ዛሬም ዘወትርም በጥላዋ ሥር እንድንከለል የምትጠራንም ለዚህ ነው፡፡ በቤቷ፣ በቅድስናው ስፍራ እንድንኖርም ታስተምረናለች፤ ትመከረናለች፡፡
ይህን የአምላካችንም የሰላም ጥሪ መስማትና ወደ ቤቱ መመለስ ደግሞ ከእኛ ይጠበቃል፡፡ የሰላም ባለቤት የሆነው ጌታችን ካለንበት ሥቃይ አውጥቶ፣ ችግራችንን ፈትቶና ከመከራ አውጥቶ በመልካሙ፣ በጽድቁ ጎዳና ይመራናል፤ እውነተኛ መንገድ እርሱ ነውና፤ ‹‹እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ›› እንዲል፡፡ (ዮሐ.፲፬፥፮) ሕዝብ ሰላም ከሆነ ሀገር ሰላም ይሆናል፤ ሀገር ሰላም የምትሆነው ደግሞ የሁሉ ፈጣሪ አምላካችን እግዚአብሔር ሲከበር፣ ሲፈራ፣ ሲመለክና ቤቱ በቅድስና ሲጠብቅ ነው፡፡