መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

ያለምንም ደመወዝ በራሳቸው ዓቅም በግብርና እየተዳደሩ ቤተ ክርስቲያንን በጥሩ ሰብእና በንጽሕና እና በቅድስና ጠብቀው ያስረከቡ እልፍ አእላፍ አበው እንዳልነበሯት ዛሬ የተሻለ ኑሮና ደመወዝ እያገኘን እግዚአብሔርን እንደቀኖናው በጥንቃቄ ማገልገል አቅቶናል” ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ

ጥቅምት ፬/፳፻፲፰ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ

የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ

የአዲስ አበባና ሐድያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የየመምሪያውና የየድርጅቱ ኃላፊዎች ፣

ከሀገር ውስጥና ከውጭ ሀገር የመጣችሁ የየሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጆችና የየክፍሉ ተወካዮች፣

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ኃላፊዎች፣

የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችና ተወካዮች

የምእመናንና የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች፣

በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ ጉባኤ የተገኛችሁ ክቡራና ክቡራት

እግዚአብሔር አምላካችን ዓመቱን ጠብቆ በከፍተኛ ጉጉት ለምንጠብቀው አርባ አራተኛው የሰበካ ጉባኤ አጠቃላይ መንፈሳዊ ዓለም ዓቀፍ ጉባኤ ስላደረሰን ክብርና ምስጋና ለእርሱ እናቀርባለን፡፡ እናንተንም እንኳን በደኅና መጣችሁ እንላለን፡፡

“ዑቁ እንከ ዘከመ ተሓውሩ ከመ ጠቢባን በንጽሕ ወአኮ ከመ ዓብዳን፤ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንደ ጥበበኞች እንዴት በንጽሕና እንደምትመላለሱ ዕወቁ” (ኤፌ.፭፥፲፭)፤ ሁሉንም መስጠትና መንሣት የሚችለው እግዚአብሔር አምላክ ጥበብን ለሰው ልጆች ሰጥቶአል፤ የሚሰጠው የጥበቡ ደረጃ የተለያየ ቢሆንም እግዚአብሔር ከጥበብ ባዶ አድርጎ የፈጠረው ግን የለም፤ የእግዚአብሔር ስጦታዎች ለፍጡራን ሲሰጡ ሊጠቀሙባቸው እንጂ እንዲሁ በከንቱ ሊያባክኑዋቸው አይደለም፡፡

ቅዱስ መጽሐፍ ስለ ጥበብ አስፈላጊነት በብዙ ቦታ ያስተምራል፤ በተለይም ጠቢቡ ሰሎሞን “ጥበብ ትኄይስ እምኲሉ መዛግብት ወኲሉ ክብር ኢመጠና ላቲ፤ ከሀብት ሁሉ ጥበብ ትበልጣለች፤ ክብርም ሁሉ አይመጣጠናትም” በማለት የጥበብ ብልጫ ተወዳዳሪ የሌላት እንደሆነች ያስገነዝበናል፤ እግዚአብሔርም ሥራውን ሁሉ በጥበብ እንደሚሠራ “ወኲሎ በጥበብ ገበርከ፤ ሁሉንም በጥበብ አደረግህ” በሚል ተጽፎ ይገኛል፤ እግዚአብሔር ሥራውን በጥበብ እንደሚሠራ፣ እኛንም በጥበብ መሥራት እንዳለብን ሲያስተምረን፣ ‹‹ኩኑ ጠቢባነ ከመ አርዌ ምድር እንደ እባብ ብልሆች ሁኑ›› ብሎናል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት!

ክቡራን የጉባኤው ተሳታፊዎች!

ዘመንና ቦታ ሳይገድበን ምንጊዜም ሥራችንን በጥበብ መሥራት እንዳለብን ቢታወቅም ዛሬ ላይ ከምን ጊዜውም በበለጠ በጥበብ መመላለስ የሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ እንገኛለን፤ የዛሬዎቹ ችግሮች በአንድ አካባቢ ብቻ ያሉ ሳይሆኑ ዓለም ዓለፍ ቅርጽ ያላቸው እንደሆኑ ታላላቅ መሪዎች ሳይቀሩ በዓለም መድረክ ላይ ስሞታ ሲያቀርቡ በዓይናችን አይተናል፤ በጆሮአችንም ሰምተናል፤ በሁኔታውም የክርስትና ሃይማኖት በአጠቃላይ በተለይም ደግሞ የኦርቶዶክሱ ወገን የችግሩ ገፈት ቀማሽ እንደሆነ እየተስተዋለ ነው፡፡

እኛም የዚሁ ወገን አካል በመሆናችን የችግሩ ቀማሽ መሆናችን አልቀረም፤ በየቀኑ ካህናትና ምእመናን ይገደሉብናል፤ አብያ ክርስቲያናት ይቃጠሉብናል፤ የእምነትና የኅሊና ነጻነት በእጅጉ የሳሳ ሆኖብናል፤ አላስፈላጊ ጫናዎችም በዝተውብናል፤ ከውጭና ከውስጥ በተቀነባበረ ስሌት የቤተክርስቲያናችንን ስም ማጥፋት የዕለት ተግባራቸው ያደረጉ አካላት ተበራክተዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ከነባሩና ረጅም ዘመን ካስቈጠረው ሰፊ ማእዷ እያበላቻቸው ያለች መሆኗን ዘንግተው እንብላሽ፣ እንዋጥሽ የሚሉዋት ወገኖች በዝተዋል፣ በእነዚህና በሌሎች ምክንያቶች አባቶች እንደልብ ተንቀሳቅሰው መሥራት የማይችሉባቸው አጋጣሚዎች እየተፈጠሩ ነው፤ የወለጋው ችግር ለዚህ በዋናነት ተጠቃሽ ነው፡፡

ታድያ እነዚህን ፈተናዎች ለማለፍ ጥበብ ያስፈልጋል፤ ነገር ግን ጥበብ መከተል ማለት ዝም ብሎ ማለፍ ወይም አይተው እንዳላዩ ሆኖ መኖር ማለት አይደለም፤ በጥበብ መመላለስ ማለት ከሁሉ በፊት ችግሮችንና የችግሮችን መንሥኤዎች በአግባቡ መረዳትና መለየት መቻል ነው፤ ከዚያም ራስን ለከፋ አደጋ በማያጋልጥ መልኩ የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም መሸጋገር መቻል ነው፤ በዚህ ዘመን እንዲህ ያለ ጥበብ መጠቀም የግድ ያስፈልጋል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት!

ክቡራን የጉባኤው ተሳታፊዎች! ቤተ ክርስቲያናችን እየተፈተነች ያለችው ከውጭ ብቻ ሳይሆን ከውስጥም ጭምር እንደሆነ መካድ የለብንም፤ ንጽሕትና ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥር የሰደደ የቅድስና ሕይወትና በፈሪሀ እግዚአብሔር የተቃኘ ሥነ ምግባር ያላት ቤተ ክርስቲያን ናት፤

በአሁኑ ጊዜ ግን እነዚህ ሁሉ ቦታቸውን እየለቀቁ ያሉ መስለዋል፤ ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ ታሪኳ ሲያስተምሩም ሆነ ሲማሩ፣ ሲመንኑም ሆነ ሲመነኲሱ፣ ሲቀድሱም ሆነ ሲያስቀድሱ ያለምንም ደመወዝ በራሳቸው ዓቅም በግብርና እየተዳደሩ ቤተ ክርስቲያንን በጥሩ ሰብእና በንጽሕና እና በቅድስና ጠብቀው ያስረከቡ እልፍ አእላፍ አበው እንዳልነበሯት ዛሬ የተሻለ ኑሮና ደመወዝ እያገኘን እግዚአብሔርን እንደቀኖናው በጥንቃቄ ማገልገል አቅቶናል፤ ምእመናንም በዚህ ምክንያት እየተሰናከሉ እንደሆነ እየተስተዋለ ነው፡፡ ሚድያውም ስሕተቶችን ወደ ውጭ በማውጣት ሰድቦ ለሰዳቢ እየዳረገን ነው፤ ይህ ሊሆን የቻለው የቤተ ክርስቲያን ሀብትና ንብረት በአግባቡ በመያዝ ለታለመለት ዓላማ ማዋል አለመቻላችን ነው፤ ይህ ችግር ባለበት ከቀጠለ ሌላ ጦስ ይዞብን እንዳይመጣ ሁነኛ ለከት ማኖር የግድ ይሆናል፡፡

የሰበካ ጉባኤ አደረጃጀት የቤተ ክርስቲያናችንን ሀብተ ጸጋ በማሳደግ ረገድ አስተማማኝ ስልት እንደሆነ በተግባር የተረጋገጠ ነው፤ ሆኖም ሲጀመር ሳለ የነበረ መነቃቃት በአሁኑ ጊዜ የቀነሰ መስሎ ይታያል፤ አሁን በቤተ ክርስቲያን ሰፊ ሽፋን ይዞ የሚገኘው የሙዳየ ምጽዋት ገቢ እንጂ የሰበካ ጉባኤ አስተዋፅኦ እንደአይደለ ሁላችንም እናውቃለን፤ በተለይም በከተሞች ውስጥ ነገሩ ጎልቶ ይታያል፡፡

ይህ የሆነበት ምክንያት ምናልባትም በየደረጃው በኃላፊነት ያለን ሰዎች ሻል ያለ ደመወዝ ስለምናገኝ የሰበካ ጉባኤው ተልእኮ ከሚፈለገው ደረጃ ላይ  የደረሰ መስሎን ይሆናል፤ ነገር ግን ከሰማንያ ከመቶ ያላነሰ የገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ መምህርና ካህን አሁንም ያለ ደመወዝ የሚኖር ነው፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከቤተ ክርስቲያኑ ሊያገኘው የሚገባ የበጎ አድራጎት የጤና የትምህርትና የማኅበራዊ ዋስትና አገልግሎት በሚጠበቀው ደረጃ ሊያገኝ አልቻለም፤ የገዳማትና የአብነት ት/ቤቶች ችግሮችም በነበሩበት የልመና ኑሮ እየቀጠሉ ነው፤ በውጤቱም በችግር የሚኖሩ ገዳማት የተዘጉ የአብነት ት/ቤቶችና አብያተ ክርስቲያናት ከተበራከቱ ሰነባብቶአል፡፡

ታድያ ይህንን ሁሉ መልክ ማስያዝና ቤተ ክርስቲያንን ለቀጣዩ ትውልድ ማሸጋገር የሚቻለው በጥበብና በጥበብ ብቻ መሥራት ሲቻል ነው፤ ይህንን ችግር መፍታት የሚያስችል ጥበብ ደግሞ በዘመናችን አለ፤ የጠፋው ቅንነቱና ፈቃደኝነቱ ነው፡፡

በየዓመቱ የምናካሄደው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ እንደነዚህ ያሉትን ችግሮች መቅረፍ የሚያስችል ካልሆነ ተሰብስበናል ማለቱ ብቻ ትርጉም ሊኖረው አይችልም፤ ስለሆነም ከዚህ በላይ የተጠቃቀሱና ሌሎችም የቤተ ክርስቲያናችን ተግዳሮቶች ካሉ በዚህ ጉባኤ በማንሣት በማየትና በመገምገም ለቤተ ክርስቲያን አሻጋሪና ጥበባዊ ውሳኔ እንዲያሳልፍ አባታዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም

ዓመታዊው ዓለም ዓቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በጸሎተ ወንጌል የተከፈተ መሆኑን በእግዚአብሔር ስም እናበሥራለን፡፡

መልካም ጉባኤ ያድርግልን!

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ !!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር !!!

አሜን!!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የአዲስ ዓመት አባታዊ መልእክት !!!

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ የ፳፻፲፰ ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓል መግባትን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሰጥተዋል፣ የቅዱስነታቸው ሙሉ መልእክት የሚከተለው ነው።

ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰንመቱ ዓመተ ምሕረት፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ኣሜን!

  • በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
  • ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
  • የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
  • በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣
  • እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያት በሙሉ፣

አምላክነቱን ኣውቀን እንድናመልከው ዕድሜንና ዘመናትን የሚሰጠን እግዚብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺህ ዐሥራ ስምንት ዓመተ ምሕረት የርእሰ ዐውደ ዓመት በዓል አደረሰን አደረሳችሁ!

‹‹ወገብረ ኵሎ ኅቡረ ወኵሎ ኣሕዛበ እምአሐዱ ዕጓለ እመሕያው ከመ ይንበሩ ዲበ ኵሉ ገጸ ምድር፤ ወሠርዐ ዕድሜሁ ወዓመታቲሁ መጠነ ይነብሩ በዘየኃሥዎ ለእግዚአብሔር፤ እመ ይረክብዎ፤ ወያደምዕዎ፤ ወኢኮነ ርሑቀ እምኵልነ፡-

ምናልባትም እየመረመሩ ያገኙት እንደሆነ እግዚአብሔርን ይፈልጉ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ እንዲኖሩ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከኣንድ ፈጠረ፤ የተወሰኑትንም ዘመኖችና ለሚኖሩበት ስፍራ ደረጃ መደባላቸው፤ ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ ኣይደለም›› (የሐ. ሥራ. ፲፯÷፳፮)፤

ፈጣሬ ፍጥረታት እግዚአብሔር ትዕይንተ ዓለምንና በውስጡ የሚገኙ ፍጥረታትን የፈጠረ አምላክ ነው፤ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት የሚታዩና የማይታዩ ተብለው በጥቅል በቅዱስ መጽሓፍ ተገልጸዋል፤

የሰው ልጅ ከፍጥረታት መካከል ሆኖ ከኣንድ ወገን የተገኘ እንደሆነ በዚህ ጥቅስ ተጽፎአል፤

የሰው ልጅ ከፍጥረታት ሁሉ የተለየ ክብርና ደረጃ እንዳለው በቅዱስ መጽሓፍ በተደጋጋሚ ተገልጾአል፤ ልዩ የሚያደርገውም ከኣፈጣጠሩ ጀምሮ ነው፤

ሰው ልዩ ፍጡር መሆኑን ከሚገለጽባቸው መካከል እግዚአብሔር በሦስትነቱ “ሰውን በኣርኣያችንና በኣምሳላችን እንፍጠር” በሚል ልዩ ኣገላለጽ መፈጠሩ፣ ኣፈጣጠሩም በእግዚአሔር መልክና ኣምሳል መሆኑ፣ በእግዚአብሔር እፍታ ሕያው ነፍስ እንዲኖረው መደረጉ፣ በሥልጣንም የፍጥረታት ሁሉ የበላይ ሆኖ መሾሙ ከሌሎች ፍጥረታት ልዩ ያደርገዋል፡፡

ከዚህ አንጻር ሰው በዚህ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ዓለም ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ነው፤ የሁሉም ገዥ ነው፤ በተለይም በዚህ ዓለም ከሰው በላይ ሆኖ የፍጡራን ገዥ የሆነ ፍጡር እንደሌለ ሁላችንም የምናየውና የምናውቀው ነው፤

በላይኛው ዓለምም ቢሆን መላእክትን ጨምሮ ሰማይና ምድርን ከነግሣንግሡ እየገዛ ያለው ሰው የሆነ ጌታ ነው፤ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ የፍጥረት ገዥ ነው፤ እሱ ሰብእናችንን በፍጹም ተዋሕዶ የተዋሓደ በመሆኑ ሰብእናችን በተዋሕዶተ ቃል ኣምላክ ሆኖ የፍጥረታት ሁሉ ገዥ ሆኖኣልና ነው፤

ቅዱስ መጽሓፍም “ወተኰነኑ ሎቱ መላእክት ወሥልጣናት ወኵሉ ኃይል፡- መላእክት፣ ሥልጠናትና ኃይል ሁሉ ተገዙለት” በማለት ይህንን ያረጋግጣል፤ ይህ እግዚአብሔር ለኛ ለሰዎች ያጐናጸፈን ግሩምና አስደናቂ ጸጋ ነው፤ ለዚህም ነው “ወሰብእ ይከብር እምኵሉ ፍጥረት፡- ሰው ከፍጥረት ሁሉ ይከብራል” ተብሎ የሚዘመረው፤

  • የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውንና ኢትዮጵያውያት!

እኛ ሰዎች የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ ሆነን እንድንኖር በእግዚአብሔር ስንፈጠር በሕይወት እንድንኖር ነው፤ እግዚአብሔር በምድር ላይ በሕይወት ይኖሩ ዘንድ ሰውን ከኣንድ ፈጠረ የሚለው መጽሓፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮም ይህንን ያመለክታል፤

ሰዎች በምድር ላይ በሕይወት እንዲኖሩ የተፈጠሩ ሆነው እያለ በሕይወት እንዳይኖሩ ማድረግ ከፈቃደ እግዚአብሔር ጋር መጋጨትን ያስከትላል፤በዘመናችን ዓለማችንን እየፈተነ ያለው ተቀዳሚ ፈተና ሰዎች በሕይወት እንዳይኖሩ የማድረግ ዝንባሌ ነው፤

እንደዚህ ዓይነቱ ዝንባሌ በዓለም ባይኖር ኖሮ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቈጠሩ ድሆች ባሉበት ዓለም ለሰው ልጅ ሕይወት ማጥፊያ የሚሆን መሳሪያ ለማምረት ኁልቈ መሣፍርት የሌለው ገንዘብ አይወጣም ነበር፤

ይህ ክፉ የዓለም ዝንባሌ እንደ ክፋት ብቻ ሳይሆን እንደ ሞኝነትም የሚያሳይብን ነው፤ማንኛችንም ሰዎች ‹‹ሰው ማጥፋት ይሻላል ወይስ ማዳን›› ተብለን ብንጠየቅ መልሳችን ምን እንደሚሆን ይታወቃል፤

ነገር ግን ኣንፈጽመውም፣ ሞኝነት የሚያሰኘውም እዚህ ላይ ነው፤ የሚጠቅመንንና የመሰከርንለትን ትተን የሚጐዳንንና፣ ያልመሰከርንለትን እንፈጽማለንና ነው፤ ስለሆነም በሕይወት እንዲኖር የተፈጠረውን ሰው በሕይወት የመኖር መብቱን ከመንፈግ መቆጠብ የኣዲሱ ዓመት ትልቁ ኣጀንዳ ኣድርገን ብንወስድ ለሁላችንም ይበጀናልና እንቀበለው እንላለን፤

  • የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን! ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት!

ሰው በሕይወት እንዲኖር በእግዚአብሔር ሲፈጠር እግዚአብሔርን የሚፈልግበትና የሚያገኝበትን ዕድሜና ዘመንም እንደተሰጠው ከተጠቀሰው ክፍለ ንባብ እንገነዘባለን፤ መቼም እግዚአብሔር ሁሉን የፈጠረ በስራ ለስራ እንደሆነ የምንስተው ኣይሆንም፤

እግዚአብሔር ዕድሜና ዘመን ለሰዎች ሲሰጥ ሊሠራበት ነው፤ ስራውም መንፈሳዊና ዓለማዊ ነው፤ ተደምሮ ሲታይ ደግሞ ለሰው ጥቅም የሚውል ነው፤

እኛ ሰዎች በተሰጠን ዕድሜና ዘመን በመንፈሳዊው ሥራችን እግዚአብሔርን ፈልገን እንድናገኝ ተፈጥረናል፤ እሱን ማግኘት የማይቻል የሚመስለን ካለንም እሱ ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም ተብለናልና በመንፈስ ከፈለግነው በመንፈስ እንደምናገኘው መጽሐፉ ያስረዳናል፤ ስለሆነም በተሰጠን ዘመን ይህንን ሥራ መሥራት ይኖርብናል፤

በሌላ በኩል ለኑሮኣችን የሚያስፈልገንን ፍጆታ በበቂ ሁኔታ እንድናገኝ ላባችንን ኣንጠፍጥፈን መስራት ይገባናል፤ ይህም ከሰራን ያለጥርጥር የምናገኘው ነው፤ ሁለቱም የጐደሉብን በኛ አስተሳሰብ፣ አሠራርና አጠቃቀም እንጂ እግዚአብሔር ሳይፈቅድልን ቀርቶ ወይም ነፍጎን አይደለም፤

እግዚአብሔር የሰጠን ምድር በልዩ ልዩ ሀብተ ጸጋ የተሞላች እንደሆነች፣ የምንረግጠው መሬትም ወደ ሀብት መቀየር እንደሚቻል የተረጋገጠ ነው፤

ነገር ግን እኛ በምንራመድበት በእግራችን ሥር ያለውን ሀብት ትተን በሩቅ ያለውን ስንመለከት ሁሉን ያጣን ሆነን በችግር ወድቀን እንገኛለን፤ በተለይም እኛ ኢትዮጵያውያን በአሁኑ ጊዜ እየተፈታተነን ያለው ይኸው የተሳሳተ እሳቤ ነው፤

ኢትዮጵያ የሁላችንም ኢትዮጵያውያን ኣድርገን በማመን በእኩልነት፣ በኣንድነትና በስምምነት ከመጠቀም ይልቅ ያ የኔ ነው ያም የኔ ነው በሚል ኣባባል ምን ያህል ዋጋ እየተከፈለ እንደሆነ እያየን ነው፤

ይህ ግለኝነት ያየለበት አስተሳሰብ ገታ አድርገን በእኩልነትና በአብሮነት የሚያሳድገንን አስተሳሰብ በእጅጉ ይጠቅመናል፤ ይህንንም የአዲሱን ዓመት ምርጥ እሳቤ ኣድርገን ብንወስድ የተሻለ መግባቢያ ሊሆን ይችላል፤ አዲሱ ዓመት በኣዲስ እሳቤ ካላጀብነው አዲስ ሊሆን አይችልምና ነው፤

ስለሆነም ኣዲሱን ዓመት መልካም በሆነ ኣዲስ ኣሳብ ፣እግዚአብሔርንና ሰውን በሚያገናኝ ቅዱስ ተግባር፣ በልማት፣ በሰላም፣ በፍቅር፣ በዕርቅና በስምምነት እንድንቀበለው ወቅታዊ ጥሪያችን ነው፤

በመጨረሻም፣ አዲሱ ዓመት ለሀገር ሰላምና ልማት፣ ለሕዝቦች ኣንድነትና ስምምነት እንደዚሁም ኣለመግባባትን በፍትሕና  በዕርቅ ለመፍታት ከልብ የምንተጋበት መልካም የስኬት ዘመን እንዲሆንልን እንጸልይ፣ በዚህም መላ ሕዝባችን ጠንክሮ እንዲሠራ ለመላ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ሁሉ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፤

እግዚአብሔር ኣምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ኣሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣

መስከረም ቀን ፳፻፲፰ .

አዲስ አበባኢትዮጵያ

ርእሰ ዐውደ ዓመት

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የ፳፻፲፯ ዓ.ም የጾመ ነነዌ የሰላምና የጸሎት ዐዋጅ መግለጫ

‹‹ቀድሱ ጾመ ወስብኩ ምህላ አስተጋብኡ ሕዝበ ሊቃውንተ ሕዝብ፤ ጾምን ቀድሱ፣ ጉባኤውንም ዐውጁ፤ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ቤት ሰብስቡ፤ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ።›› (ኢዩ.፩÷፲፬)

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ አምስት ቁጥር ፻፷፬ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ከጥቅምት ፲፩ እስከ ጥቅምት ፳ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም. ድረስ መደበኛ ስብሰባውን ሲያካሂድ ሰንብቷል፡፡

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

የአቋም መግለጫ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የ፵፫ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ዓለም አቀፍ መደበኛ ጉባኤ የአቋም መግለጫ

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ዐሠርቱ ወሰብዓቱ ዓመተ ምሕረት