ነቢያት ለምን ጾሙ?

ኅዳር ፲፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

የአዳም ዘር በሙሉ በኃጢአት ባርነት ተይዞ፣ ለ፶፻፭፻ ዓመታት በፍዳ አረንቋ ውስጥ ሲኖር ተስፋ ሲያደርግ የነበረው የእግዚአብሔር አብ ልጅ እግዚአብሔር ወልድ ለአዳም የገባለትን የመዳን ቃል ኪዳን ነው፡፡ ይህም ይፈጸም ዘንድ ነቢያት አስቀድሞ ትንቢት ተናግረዋል፡፡

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስለ መወለዱ ፥ ወደ ግብፅ ስለ መሰደዱ ፥ በባሕረ ዮርዳኖስ ስለ መጠመቁ ፥ ብርሃን በሆነው ትምህርተ ወንጌል ጨለማውን ዓለም ስለ ማብራቱ ፥ ለሰው ልጆች ድኅነት ጸዋትወ መከራ ስለ መቀበሉና ስለ መሰቀሉ ፥ ስለ ትንሣኤው ፥ ስለ ዕርገቱና ስለ ዳግም ምጽአቱ ትንቢት ተናግረው አላቆሙም፡፡

ነቢዩ ዳዊት “እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም” በማለት ሲማጸን (መዝ.፻፵፫፥፯) ነቢዩ ኢሳይያስ ደግሞ “እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች፥ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” በማለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም እንደሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ (ኢሳ.፯፥፲፬) በዚህም የተስፋ ቃል “ኃይልህን አንሳ፤ እጅህንም ላክ” በማለት ነቢያት እየተማጸኑ ጾመዋል፡፡

የነቢያት ጾም (የገና ጾም) ከኅዳር ፲፭ ጀምሮ ለ ፵፫ ቀናት የሚጾም ሲሆን ፋሲካው (ፍቺው) በልደት በዓል ነው፤ ይህም ጾም በዘመነ ብሉይና በዘመነ ሐዲስ ቅዱሳንና ምእመናን ጾመውታል፡፡ እኛም አምላካችን ቸርነቱን እንዲያበዛልን፣ ከፈተና እንዲያወጣን፣ ወቅታዊውን ሀገራዊ ችግር ይፈታልን ዘንድ፣ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ እንዲሠውረን ጾሙን እንጹም!

የጌታችን ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና የቅዱሳን ነቢያት ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ አሜን!