ሐምሌ 23 ቀን 2010 ዓ.ም የተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ምልዓተ ጉባኤ በአባቶች ላይ በተለያየ ወቅት ያስተላለፈውን ቃለ ውግዘቱን አንስቷል

ሐምሌ 23 ቀን 2010 ዓ.ም የተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ አስቸኳይ ምልዓተ ጉባኤ በአባቶች ላይ በተለያየ ወቅት ያስተላለፈውን ቃለ ውግዘቱን አንስቷል፡፡ሙሉ ውሳኔው እንደሚከተለው ነው

   የአባቶች አንድነት ላይ የተሰጠ  የደስታ መግለጫ!

       

ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ ከእቶነ እሳት በወጡበት በብሥራተ መልአክ በቅዱስ ገብርኤል የመታሰቢያ ዕለት የኢትዮጵያ አርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  አባቶች  አንድ ሆነዋል፡፡በዚህም የምእመናን ተስፋ ለምልሟል፡፡የጥል ግድግዳ ፈርሷል፡፡ይህ ታላቅ መንፈሳዊ ተግባር የተፈጸመበት ዕለት ለቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ የደስታ ዕለት ነው፡፡ይህ ዕለት ሰይጣን ቤተ ክርስቲያንን ለመዋጋት ጥይቱን የጨረሰበት፤ዝናሩን አራግፎ ባዶ እጁን የቀረበት ነው፡፡ዕለቱ የሰይጣን ጥርሱ የረገፈበትና የቤተ ክርስቲያን ብርሃን ለዓለም የተገለጠበት በመሆኑ የቤተ ክርስቲያን የምስራች ቀን ነው፡፡

ለዚህ ዕለት ደርሶ የተገኘውን ዕርቅ አይቶ የማይደሰት ቢኖር ዲያብሎስ ብቻ ነው፡፡ዕርቁ እውን እንዲሆን መለያየት እንዲወገድ፤የተፈጠረው ክፍተት መፍትሔ እንዲያገኝ ያደረገ እግዚአብሔር ይመስገን በማለት በቅን ልቡና የተቀበላችሁ ቅዱሳን ፓትርያርኮቻችን የፈረሰውን አንድነት በዘመነ ፕትርክናቸሁ ለመጠገን ፤የተለያየውን አንድ ለማድረግ፤የሻከረውን ለማለስለስ ያበቃችሁ እግዚአብሔር ይመስገን !

ከቅዱሳን አባቶቻችንና ከቅዱስ ሲኖዶስ የተቀበላችሁትን አደራ ከዳር ለማድረስ አንድ ጊዜ  አሜሪካ ሌላ ጊዜ ኢትዮጵያ በመመላለስ የደከማችሁ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና  በየአገሩ የምትገኙ የዕርቀ ሰላም ኮሚቴ አባላት እንኳን የድካማችሁን ፍሬ ለማየትና “ዕርቅ የሚያደርጉ ብፁዓን ናቸው፤ እነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና” (በማቴ፭፥፱) የተባለው ተፈጽሞ ለማየት አበቃችሁ!

ዕርቁ ለቤተ ክርስቲያን፤ ለምእመናን አንድነት እንዲሁም ለሀገር ሰላም የሚኖረውን ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑን ተመልክተው ለተግባራዊነቱ የሚችሉትን ሁሉ ላደረጉት ለኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስተር ለክቡር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ከፍተኛ ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ በመጨረሻም ዕርቁ ተግባራዊ እንዲሆን በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን ስትጠይቁ ለኖራችሁ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፤መምህራን ፤ገዳማውያንና ምእመናን  እንኳን ይህን የአባቶችን የአንድነት ቀን ለማየት አበቃችሁ፤አበቃን በማለት ማኅበረ ቅዱሳን በራሱና በአባላቱ ስም ደስታውን ይገልጻል!

ይህ ደስታ የቤተ ክርስቲያን ታላቅ በዓል በመሆኑ ቤተ ክርስቲያናችን በምታደርግልን ጥሪ መሠረት ሁላችንም ምእመናን በአቀባበሉ ሥርዓት በመሳተፍ ፤የድርሻችንን እንድንወጣ ማኅበረ ቅዱሳን ጥሪያውን ያስተላልፋል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!

ሐምሌ 20 ቀን 2010 ዓ.ም

 

የአባቶች ዕርቀ ሰላም መፍጠር፤ ለቤተ ክርስቲያንሐዋርያዊ አገልግሎትና ለሀገራዊ መግባባት ወሳኝ ሚና አለው!

 

በዮሐንስ አፈወርቅ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሠረቷኗ ጉልላቷ ክርስቶስ በመሆኑ የሰላም ደጅ ናት፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ በጻፈው መልእክቱ “የሰላምም ጌታ ራሱ በሁሉ መንገድ ዘወትር ሰላምን ይስጣችሁ፡፡ ጌታ ከሁላችሁ ጋር ይሁን፡፡” (2ኛ ተሰሎ 3፡16) እንዳለ በክርስቶስ ሰላም እየተጠበቀች አንድነቷ ላይ የሚያጋጥሟትን ፈተናዎች ሁሉ እየተቋቋመች አገልግሎቷን በማስፋፋት ምእመናንን ትጠብቃለች፡፡ አባቶችም ከቤተ ክርስቲያን የተቀበሉትን አደራ ተግተው በመጠበቅ መንጋውን በክርስቶስ ሰላም ማጽናት ይኖርባቸዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቁ ዘንድ ለመንጋውና ለራሳቸውም መጠበቅ ጥንቃቄ ያደርጉ ዘንድ የእግዚአብሔር ቃል ያስተምረናል፡፡ «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ፣ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጐ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ» ሐዋ 20፡28
በመሆኑም የቤተ ክርስቲያን ጭንቀቷ ለጊዜያዊውና ለሚያልፈው ሳይሆን ለዘላለሙ፣ ለምድራዊው ሳይሆን ለሰማያዊው ሕይወት በመሆኑ፣ ዓለሙ ከሚከፋፈልበት የዘር፣ የጐሳ፣ የቋንቋና የርዕዮተ ዓለም አመለካከት ልዩነቶች የራቀች መሆን ይጠበቅባታል፡፡ የመንፈስ ልጆቿን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ወልዳ ከማይጠፋ ዘር በክርስቶስ ሥጋና ደም አንድ አድርጋ የምትመራ ለአንድና ለማያልፍ የእግዚአብሔር መንግሥት የምትሠራ ነፍሳትንም ለዚህ ክብር የምታዘጋጅ ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጉልላቷ አንድ በመሆኑ፣ ልጆቿ ሁሉ በእግዚአብሔር ቅዱስ መንፈስ የአንድ አካል ብልቶች እንዲሆኑ ትሠራለች፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት እንቅፋት የሚሆኑ ነገሮች ሁሉ፣ ትእዛዛተ እግዚአብሔርን የሚፃረሩ በመሆናቸው፤ ለጥላቻዎችና መለያየቶች መንስኤ የሆኑ ነገሮችን አጥርቶ ማየትና መፍትሔ ለመስጠት መሄድ ሕገ እግዚአብሔርን መፈጸም ነው፡፡
ጥላቻዎችና መለያየቶች ሰላመ ቤተክርስቲያንንና ሕዝበ እግዚአብሔርን የሚያውኩ በመሆናቸው፣ በእነዚህ አትራፊ የሚሆነው፣ ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ብቻ እንጂ፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ተከታዮቿ የሆኑት ሕዝበ እግዚአብሔር አይደሉም፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓለሙ የሚለያይባቸውን ነገሮች የምታወግዝ እንጂ፣ አካሏን ለሚለያይና ፍቅርን ለሚያደበዝዙ ክፍተቶች አሳልፋ መተው የለባትም፡፡ እንኳን የራስን አካል ቀርቶ ቃሉ ጠላትንም መውደድ እንዲገባን ያስተምረናል፤ “እኔ ግን እላችኋለሁ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ የሚረግሙአችሁን መርቁ ለሚጠሏችሁም መልካም አድርጉ ይላልና—“ (ማቴ 5፡44-45) ክርስቲያኖች ሁሉ እውነተኛ ጨው ሆነን ዓለሙን ማጣፈጥ ሲገባን ይህን ቸል ብለን መንጋውን ለዓለሙ ክፉ ሐሳብ፤ መለያየትና ለዘረኝነት መራራ ፍሬ አሳልፈን እንዳንሰጥ መጠንቀቅ ይገባናል፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት ለዓለሙ ጨው ሆነው የወንጌልን ፋና ያበሩት፣ በአንድ ልብ ሆነው በጸሎትና በጾም በመትጋታቸው የመንፈስ ፀጋን በመጎናጸፋቸው ነው እንጂ፤ እርስ በርሳቸው በመለያየት አይይደለም፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፡- በአጥቢያዎች፣ በወረዳና በአህጉረ ስብከት የተደራጀች ስትሆን፤ እነዚህ መዋቅሮቿ፣ ጉልላቷና መሠረቷ የሆነውን የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዛት፣ መርሓቸው አድርገው የሚሄዱ እንጂ «ከእርሱም የተነሣ አካል ሁሉ እያንዳንዱ ክፍል በልክ እንደሚሠራ፣ በተሰጠለት በጅማት ሁሉ እየተጋጠመና እያተያያዘ፣ ራሱን በፍቅር ለማነፅ አካሉን ያሳድጋል» ኤፌ 4፡16 ተብሎ የተጻፈውን በመቃረን፣ በየራሣቸው የሚመሩ፣ የማይነጋገሩና የማይተጋገዙ፣ አንዱ ለሌላኛው ግብኣት የማይሆኑ ብልቶች ሆነው በየግላቸው የሚጓዙ አይደሉም፡፡
ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት የሚያርቁ ምክንያቶችና ክስተቶች፣ የክርስቶስ አካል በሆነችው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሉዓላዊነት ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥሩ ስለሆኑ፤ እነዚህን ምክንያቶችና ሁኔታዎች እያንዳንዳችን ትኩረት ሰጥተን መመርመርና ማየት ይገባናል፡፡ በመሆኑም ፈራጅ በመሆን ብቻ ወይም አጋጣሚውን ለየግል ፍላጐታችን መጠቀሚያ በማድረግ፡- መለያየትንና ጥላቻን የምናበረታታና የምናሣድግ፣ በአጠቃላይም ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የማይጠቅሙ ነገሮች እድል እንዲያገኙና ተደብቀው እንዲያድጉ፣ በቸልተኝነት ቀዳዳ የምንፈጥር እንዳንሆን መጠንቀቅ ይገባናል፡፡
ዓለሙ በራሱ ፍልስፍናና ምድራዊ ጥበብ፣ ሕግጋተ እግዚአብሔርን ባለመጠበቅ፣ የቅድስት ቤተክርስቲያንን ህልውና ለራሱ በሚመቸውና በሚጠቅመው መንገድ እንዲሆንለት ይሠራል፡፡ ጥበብ ምድራዊን መርሑ አድርጐ የሚሄድ ሰው ወይም አካል፡- የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሉዓላዊነት ዕውቅና ሰጥቶ ከመጠበቅ ይልቅ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለእርሱ ተገዢና ዓላማ ማስፈጸሚያ እንድትሆንለት ይሻል፡፡ በዚህ ጊዜም የቅድስት ቤተክርስቲያን አባቶች በጥበብ ምድራዊ አመለካከት የሚገጥማቸውን ፈተና በጸሎት ተግተው፣ እየተመካከሩ ድል ያደርጉታል እንጂ፣ ፈተናው ከራሳቸው አልፎ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አንድነት፣ ህልውናና አገልግሎት እንዲገዳደር ዕድልና ቀዳዳ የሚፈጥሩለት አይሆኑም፡፡
የቤተ ክርስቲያንን አድነት ለማስጠበቅ አባቶች፡- ፈቃድ፣ አቅጣጫ፣ ኃይልና ጥበብ የሚጠይቁት፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሪ ከሆነው ከመንፈስ ቅዱስ እስከሆነ ድረስ፤ የዓለሙን ፍላጐትና ሐሳብ የሚከተል፣ በእርሱም ተጠልፎ የሚወድቅ አይደለም፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች ሕይወትና ሥራ ሙሉ ለሙሉ የእግዚአብሔርን ክብርና የቤተክርስቲያንን ደኅንነት ቅድሚያ ሰጥቶ ለማረጋገጥ የቆመና ቁርጠኝነት ያለው ሲሆን፤ የዓለሙ ፍላጐት፣ ተፅዕኖ ሊያሳርፍበት አይገባም፡፡
የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት፡- በጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሠረትነት ላይ የታነፀ፣ መንገዱም፡- ግልፅ፣ አንድና የቀና እንጂ፤ ለግል አመለካከትና ፍላጐት ተገዢ የሚይሆን፤ በፈለግን ጊዜ የምንሄድበት? ባልፈለግን ጊዜ ደግሞ መዝጋትም ሆነ መገደብ የምንችለው አይደለም፡፡ ይህ ደግሞ «ማንም እራሱን አያታል፤ ከእናንተ ማንም በዚች ዓለም ጥበበኛ የሆነ ቢመስለው፣ ጥበበኛ ይሆን ዘንድ ሞኝ ይሁን» 1ቆ 3፡18 ተብሎ እንደተጻፈው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ህልውና የሚፈታተኑ ነገሮችና ሐሳቦች በሚፈጠሩበት ጊዜ፣ በመግባባትና በመተማመን ለመፍታት መሄድ ይገባል እንጂ፣ በራሳችን ጥበብ ጌታችን በሥጋና በደሙ ለመሠረታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ሰላም መጠናከር አስተዋጽኦ ለማያደርጉ ሁኔታዎች አሳልፈን የምንሰጥ እንዳንሆን መጠንቀቅ ይገባናል፡፡
አባቶች የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሰላም፣ ሉዓላዊነትና አንድነት ጠንክረው የሚያስከብሩ በሚሆኑበት ጊዜ፣ ምእመናን ለፈተና ባለመጋለጥ ጸንተው በአጸዷ ውስጥ ለመኖር ያግዛቸዋል፡፡ በዓለሙ ያሉ ሰዎችም፣ ለአባቶች ክብር እንዲሰጡ ያደርጋቸዋል፡፡ አባቶች ሲናገሩ ተደማጭነትን፣ ሲመክሩ ደግሞ ተሰሚነትን ከሕዝቡ ሁሉ እንዲያገኙ ይረዳቸዋል፡፡ «የራሷ ሲያርባት የሰው ታማስል» የሚለው አባባል ሳይጠቀስባቸው፣ ከራሳቸው በመትረፍ፣ በሀገሪቱ ችግሮች አፈታት ላይ ከፍ ያለ ቦታና ተፈላጊነት ያላቸው እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል፤ ክብርና ሞገስም ያስገኝላቸዋል፡፡ ብዙዎችን በፍቅር መሸምገል የሚገባው እርሱ ለሽምግልና አስቸጋሪ ሊሆን አይገባም፡፡ ክርስትና በተግባር የሚታይ ሕይወት ነውና፡፡
ቤተ ክርስቲያን አንዲት ሆና እያለች «የውጪ እና የሀገር ውስጡ ሲኖዶስ» በሚል ሐዋርያዊ አገልግሎቷና የምእመናን አስተዳደሯ እርስ በርሳቸው በማይመካከሩና አንዱ ለሌላኛው ዕውቅና በማይሰጣጡ አካላት ለመምራት ሲኬድ የቆየ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና በምእመናን ሕይወት ላይ ከፍተኛ ችግር ፈጥሮ ቆይቷል፡፡ በመሆኑም እያንዳንዳችን ለችግሩ መፈጠር በቀጥታ ምክንያት ላንሆን ብንችል እንኳ፤ ከክስተቱ በኋላ ከትእዛዛተ እግዚአብሔርና ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አንጻር ተመልክተን ለተፈጠረው ችግር መፍትሔ ለመስጠት በሚገባው መጠን ያህል ያልሄድን፤ ለቅድስት ቤተክርስቲያን አንድነት ቅድሚያ ባለመስጠት በቸልተኝነት ሁኔታው እየተባባሰ እንዲሄድ ያደረግን፤ ወይም ችግሩን መንፈሳዊ ከሆኑ አቅጣጫዎች ይልቅ፣ ዓለማዊና ግላዊ ከሆኑ ነገሮች አንፃር ስንመለከተው የቆየን ከሆነ፤ ለተፈጠረው ችግር የሚመለከተን ሁሉ ከሚጠበቅብን አንፃር፣ ባለድርሻዎች ናችሁ ብንባል፤ ቢያንሰን እንጂ የሚበዛብን አይሆንም፡፡
በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መለያየት ምክንያት በውጭ ያሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አድባራት፡- በሀገር ውስጥ ባለው ሲኖዶስ የሚመሩ፣ በውጭ ሀገር የተቋቋመውን ሲኖዶስ እንደግፋለን በሚሉና ከሁለቱም ሳይሆኑ ገለልተኛ ነን በሚሉ ሦስት ቡድኖች ተከፋፍለው የሚገኙ ሆነዋል፡፡ የዚህ ሁሉ ክፍፍል መንስኤው፣ የተፈጠረውን ችግር በወቅቱ ሃይማኖታዊ በሆነ መንገድ ፈቶ መሄድ ባለመቻሉ፣ ማለትም የአንድነት አለመኖር ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል ግልጽና የታወቀ ነውና፣ በመንፈሳዊነት ማሸነፍና መሸናነፍ ባለመቻሉ፣ ዓለማዊ የሆኑ ፍላጐቶችና ተፅዕኖዎች አይለውና ተሰሚነት አግኝተው በመቆየታቸው ነው፡፡ አሁንም ይህ መከፋፈል ካልተገታ፣ አሁን ካለው እያደገ በመሄድ፣ ብዙ ውስብስብና አስፈላጊ ያልሆኑ ሁኔታዎችን ሊፈጥር ይችላል፡፡
የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን ዘመኑን የዋጁ ካልሆኑ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ጉዳዮች፣ ዓለማዊ የሆኑ ፍላጐቶችና ተፅዕኖዎች ምን ጊዜም መፈታተናቸው የማይቀር ነው፡፡ በዚህ ጊዜም፡- ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰላም፣ አንድነትና ህልውና ጠቃሚ የሆኑ ነገሮችን እየወሰድንና እየተባበርን የቅድስት ቤተክርስቲያን አንድነት የተጠናከረ፣ አገልግሎቷ የሰመረ፣ ምእመኖቿ በመንፈስ ቅዱስ መሪነትና በማንኛውም አቅም የተሰናሰሉና የጠነከሩ፣ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት ያላቸው እንዲሆኑ፣ ዕንቅፋቶችን ሁሉ ማስወገድ እንደየድርሻችን የሁላችንም ተግባር ነው፡፡ ይህንን መፈጸም አባቶችና ምእመናን ከራሳቸው በማለፍ ለሀገሪቱ ዕድገትና ሰላም ድርሻቸው የላቀ እንዲሆን፤ ባጠቃላይም የሀገርን ችግር በመፍታቱ በኩል የሚኖራቸው ተፈላጊነትና ድርሻ ከፍ ያለ ደረጃ እንዲኖረው ያደርጋል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውጪ ሀገር ካሉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር መግባባት እንዲኖር በተለያዩ ጊዜያት የዕርቀ ሰላም ልዑካንን በመላክ፣ በውጭ ሀገር ያሉ አባቶችም ለድርድር ፈቃደኛ በመሆን፣ ውይይቶች እየተጀመሩ እልባት ላይ ሳይደረስ፣ እንዲሁ ይቀሩ የነበረ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በቅርቡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በጥቅምት 2ዐ1ዐ ዓ.ም. ባደረገው መደበኛ ጉባኤው፣ አጀንዳ ቀርጾ ካስተላለፋቸው ውሳኔዎች መካከል፡- በውጭ ሀገር ካሉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር ተጀምሮ የነበረው የዕርቀ ሰላም ድርድር ቀጥሎ መፍትሔ እንዲያገኝ የሚለው አንዱ ነው፡፡ ነገሩ ሁለት ዐሥርት ዓመታትን ያሳለፈ ስለሆነ፣ እንደ ጉዳዩ አሳሳቢነት በፍጥነት እየተሄደበት ነበር ባይባልም፣ ውሳኔውን ተግባራዊ ለማድረግ በቋሚ ሲኖዶሱ አስፈላጊው ዝግጅት ሲደረግበት ከቆየ በኋላ፣ በአሁኑ ሰዓት ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለሚመለከታቸው አካላት ግልጽ ተደርጐ፣ በሁለቱም ወገን ተወያይ የሆኑ አባቶች እና የዕርቀ ሰላም ኮሚቴው ለዝግጅቱ ደፋ ቀና በማለት ላይ ይገኛሉ፡፡
የምንስማማውና ዕርቅ የምናደርገው፡- ያስቀየምንና የተቀየምን፣ የበደልንና የተበደልን፣ ይቅር ልንልና ልንባባል ነው፡፡ በአባቶች መካከል ለተፈጠረው አለመግባባት ዕርቀ ሰላም የምናደርገው በሐዋርያት ሥራ 2ዐ፡28 እንደተገለጸው፣ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአባቶች የሰጠው የኖላዊነት ተግባር በአግባቡ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ በዚህም፡- ምእመናን ወደ ለመለመው መስክ ሊመራቸው የሚገባ ጠባቂ በማጣት ለነጣቂ ተኩላ ሳይጋለጡ፤ በአንድ በረት ውስጥ ተጠብቀው፣ የመንግሥተ ሰማያት ወራሾች ይሆኑ ዘንድ ለማስቻል፣ ዕንቅፋት የሚሆኑ ነገሮችን ጊዜና ፋታ ሳይሰጡ ማስወገድና ማስተካከል የትጉህ እረኛ ተግባር ነው፡፡
ከዚህ አኳያም፡- የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶች የዓለሙን ክብርና ጥቅም ንቀው የሚተጉ ናቸውና፤ በድርድራቸው ላይ የሚያስቀድሙት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍላጐትና ህልውና ስለሆነ፤ መግባባት የማይችሉባቸው ነጥቦች ይኖራሉ ተብሎ አይጠበቅም፡፡ አባቶች ተለያይተው በመቆየታቸው አንዳቸው በሌላኛው ላይ የሚያነሷቸው ነጥቦች ሊኖሩ ቢችሉ እንኳ፣ ለቤተ ክርስቲያን ዕድገትና ህልውና ተፃራሪና ድብቅ የሆነ ነገር በመካከላቸው የሌለ እስከሆነ ድረስ፣ ይቅር ለመባባል በግንባር ቀደምትነት መቀመጥ ከሚገባቸው የጋራ መርሖዎች (የማስማሚያ ነጥቦች) በተጨማሪ፡- በቀጣይ መስተካከልና መታረም ያለባቸውን ቀሪ ዋና ዋና ነገሮች ርእሰ ጉዳይ አስቀድሞ ለይቶ በጥቅሉ በመያዝ፣ ከይቅር መባባሉ በኋላ በአደራዳሪዎች አማካኝነት በዝርዝር በመነጋገር እየፈቱ ለመሄድ፣ ከወዲሁ ሥርዓት ማበጀት አጋዥነት ያለው ነው፡፡ ርእሰ ጉዳያቸው በቅድሚያ ተመዝግቦ በቀጣይነት ለሚነሡ ነጥቦች ሁሉ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕግና ሥርዓት፣ ገዢነትና መሪነት ያለው በመሆኑ፤የዕርቀ ሰላሙ ሂደት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያልሆነ፣ የግልም ሆነ የቡድን ፍላጐት፣ አቋምና አካሔድ ጥላ ሊያጠላበት የሚችል አይደለም፡፡ዋናው ነገርም ዕርቀ ሰላሙን አጽንቶ ለመሄድ፣ በልዩነቱ ጊዜ ውስጥ የተፈጠሩ መታረም፣መታየትና የጋራ መደረግ ያለባቸውን ሁኔታዎችና አሠራሮች፣ከሁሉም ወገን ሰብስቦ፣በአደራዳሪ ሽማግሌዎች አማካኝነት ቅቡልነት ያለው አቅጣጫ እንዲያዝባቸው ማድረግ ነው፡፡
ስለ ዕርቀ ሰላሙ አስፈላጊነት፣ የአፈጻጸም ቅደም ተከተል፣ ስለ ምእመናንና የካህናት ድርሻ፣ በደንብ ታስቦበት በተዘጋጀ ሁኔታ፣ በየጊዜው በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች ሂደቱ ስለሚገኝበት ደረጃ መግለጫዎችንና መረጃዎችን መስጠት፣ የዕርቀ ሰላም ኮሚቴው ተግባር ለውጤቱም አጋዥነት ያለው ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በሁለቱም ወገን ለመነጋገርና በመሃል ላይ ሆኖ ለማነጋገር የምንቀርብ አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎችም፣ ከዚህ በፊት ተጀምረው የነበሩ ውይይቶች ውጤት ያላመጡት ለምንድን ነው? በሁለቱም ወገኖች አቀራረብ ላይ የነበረው ጠንካራና ደካማ ጐን ምን ነበር? አሁን በቀጣይ ለሚደረገው ምክክር፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት መጠናከር ሲባል በእኔ/በእኛ በኩል፣ ተስተካክሎ መቅረብ የሚገባው አቋም ምንድን ነው? ብሎ በተለያዩ የአማራጭ አቅጣጫዎች አስቀድሞ በግልና በቡድን ደረጃ ማየት፣ መዘጋጀትና መሥራት አስፈላጊ ነው፡፡
ሰላመ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ሲል ትልቅ ዋጋ የከፈለበት ሀብተ ክርስትናችን ስለሆነ፣ የምናጸናው አባቶችና ምእመናን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ህልውና በእውነት በመትጋት በአንድነት ሆነን እንደየድርሻችን አገልግሎቷን ስንፈጽም ነውና፤ ዕርቀ ሰላሙ ጊዜ የሚሰጠው አይደለም፡፡ በተለይም መለያየትን መግቢያ ቀዳዳው በማድረግ ጠላት ዲያብሎስ የራሱን ተልዕኮ ለመፈጸምና ለማስፈጸም ወደ ኋላ አይልምና፤ ዕርቀ ሰላሙን ዳር ለማድረስ ባለፉት ዓመታት ውጤታማ መሆን ባይቻልም፤ ከሚመጣው 2ዐ11 ዓ.ም. መቅደም መቻል ብልህነት ነው፡፡ ስለሆነም ኅብረታችን የቤተ ክርስቲያንን ተልእኮ ከሚያፋጥኑ ጋር እንጂ፤ በውስጧ ሆነው ከሚቦረቡሯት የተሐድሶ መናፍቃን ጋር አይደለምና፤ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጪ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር፣ ሐዋርያዊ አገልግሎቷን፣ አንድነቷንና ዐቅሟን ለማጠናከር የሚረዱ ነገሮችን ለመፈጸም፣ ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጐ መንቀሳቀስ ዘመኑን መዋጀት ነው፡፡
የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ዐቅም እንዲጠናከር በተቻለው መጠን እየሠራ ያለው ማኅበረ ቅዱሳንም፣ በአባቶች መካከል ተፈጥሮ መፍትሔ ሳይሰጠው የቆየው መለያየት፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አይጠቅምም በማለት አቋሙን ሲገልጽ ቆይቷል፡፡ ለምሳሌም በሐመር መጽሔት ላይ ብቻ ካስተላለፋቸው መልእክቶች መካከል፣ ይህን ጉዳይ በተመለከተ ከወጡት ላይ የተወሰኑትን ብንመለከት፡- በ1999 ዓ.ም. ሐመር 15ኛ ዓመት ቁጥር 1 የጥርና የካቲት ዕትም ላይ፣ ከቅርብ ዓመታት በፊት በ2ዐዐ5 ዓ.ም. ላይ ደግሞ በሐመር 2ዐኛ ዓመት ቁጥር 5 መስከረም ወር ዕትም ላይ «ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነት፣ ዕርቅና ሰላም መሠረት ናቸው» በሚል ርእስ እንዲሁም በሐመር 2ዐኛ ዓመት ቁጥር 6 የጥቅምት ወር ዕትም ላይ፡- ወቅቱ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ከዚህ ዓለም በሞት በመለየታቸው ምክንያት በምትካቸው ሌላ ፓትርያርክ ለመሾም ጥረት እየተደረገበት የነበረ ጊዜ በመሆኑ «ከሁሉም ነገር በፊት ዕርቀ ሰላም፣ ማሠራቱ የተረጋገጠለት ሕገ ቤተክርስቲያንና የምርጫ መመሪያ ያስፈልጋል» በማለት መልእክት አስተላልፏል፡፡ አሁንም ቢሆን ማኅበሩ ዕርቀ ሰላሙ የተሳካ እንዲሆን ጽኑ የሆነ ፍላጐት ያለው ስለሆነ፤ የሚችለውን ድጋፍ ለማድረግና በአባቶች የሚታዘዘውን በዐቅሙ ለመፈጸም ዝግጁ መሆኑን ይገልጻል፡፡
በአጠቃላይም፡-
1. የዕርቀ ሰላሙ ድርድር የሚጀመረው በጸሎትና በአባቶች ቡራኬ በመሆኑ፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም መለያየቱ ዓመታትን በመውሰዱ ላይ እያዘነ ስለሆነ፤ የሚታረቁና የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው ተብሎ በተጻፈው መሠረት እኛ ፈቃደኞችና ቁርጠኞች እስከሆን ድረስ፣ ፈቃደ እግዚአብሔር የማይለየን ስለሆነ፣ ዕርቀ ሰላሙ ይሳካል ብሎ በሙሉ ልብ መጀመር፡፡
2. ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሀገሪቱ ሰላምና አንድነት ብዙ እንዳላበረከተች ሁሉ፤ አጀንዳ ሁኖ የሚገኘውን ይህን የራሷን ጉዳይ ሳትፈታ መቆየቷ፣ የሰላም ባለቤት የሆነውን እግዚአብሔር የማያስደስት፣ ያላትን ክብርና ዝና ዝቅ የሚያደርገው ስለሆነ፤ በሀገራችን ውስጥ ሲንፀባረቅ ለቆየው የመለያየት መንፈስ፣ እኛም በየፊናችን አስተዋጽኦ አላደረግንም ወይ? ብሎ ራስ ራስን መጠየቅ፡፡

3. ዕርቀ ሰላሙ፣ በውጭ ሀገርና በሀገር ውስጥ ባለው ሕዝበ ክርስቲያን በጉጉት የሚጠበቅ ቢሆንም፤ ከዚህ በፊትም ከ2 ጊዜ በላይ የተደረጉ ጥረቶች ውጤታቸው እና ችግራቸው ምን እንደሆነ ሳይታወቅ እንዲሁ የቀረ ነው፤ በመሆኑም በፊታችን ሐምሌ 2010 ዓ.ም ባለው ድርድር፣ ዕርቀ ሰላም ላይ፣ መድረስ አለመቻል ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ ዕርቅና ሰላም የከፈለልንን ዋጋ እንደቀላል ማየት ነው ብሎ በማመን፣ ዕርቀ ሰላሙ ሳይቋጭ ከተያዘው የድርድር ጊዜ (ሐምሌ 2010 ዓ.ም) ማለፍ የለበትም ብሎ መነሣት፡፡
4. ዕርቀ ሰላሙ፡- ሙሉ ለሙሉ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ በመሆኑ፣ ከቅድስት ቤተክርስቲያን ጥቅም አንፃር የሚታይና የሚመዘን እንጂ፣ በጉዳዩ ዙሪያ ካሉ፣ የግል ፍላጐቶች፣ አመለካከቶችና አቋሞች አንፃር እንዲመራ የሚተው አለመሆኑን ማመንና መቀበል፡፡ “ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር” እንዲል በዚህ ወቅት ሁሉም ሰው ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ መነሣቱ እውነትም የይቅርታና የሰላም መምጫ ጊዜው ደርሶ ነው ብሎ በቅንነት መነሣት ይገባል፡፡
5. በአባቶች መካከል ለድርድር የሚቀርቡ ሐሳቦች እና ድርድሩ የሚመራበት መንገድና ስልት፣ ለቅድስት ቤተክርስቲያን ጠቃሚ የሆነ ነገር ማስገኘት የሚችል መሆኑን ማረጋገጥ ስለሚገባ፤ የተሻለውን እየተስማሙ መምረጥና መያዝ፣ ጥሩ መነሻ የሌለውን ሐሳብ ከዚህ ወገን ከዚያ ወገን የመጣ ነው ሳይባል፣ ከላይ በተራ ቁጥር 4 ከተገለጸው አኳያ ገንቢ የሆኑ ሐሳቦችና አቅጣጫዎች እየቀረቡበት፣ ግትር ሳይሆኑ፣ በሁሉም የባለቤትነት ስሜት እንዲዳብር፣ ነፃ ሆኖ መቀበልና ማንሸራሸር፡፡
6. በሁለቱም ወገን ተደራዳሪ የሚሆኑ አባቶች፣ በድርድሩ ላይ የሚነሱ ሐሳቦችና የማስማሚያ ነጥቦች ቅቡልነት ያላቸው መሆኑን በማረጋገጥ ይሁንታ የሚሰጡት፤ ከላይ በተራ ቁጥር 4 ላይ ከተገለጸው ዓላማ አንጻር እንጂ፣ ሲንፀባረቅ ከቆየና ቀደም ብሎ ከተያዘ አቋም አኳያ ጽንፍ በመያዝ እንዳይሆን ራስን መፈተሽ፡፡
7. ውጭ ሀገርም ሆነ ሀገር ውስጥ ያለው ሕዝበ ክርስቲያን ዕርቀ ሰላሙን በጉጉት የሚጠብቀው ስለሆነ፤ መስማማት ያልተቻለባቸውን ነጥቦች አደራዳሪዎች ለይተውና ቀርፀው በማቅረብ ላለመስማማት የተያዙትን አቋሞች ያንፀባረቋቸው ወገኖች፣ የገለጿቸውና የእነሱ መሆናቸውን በቅድሚያ እንዲያረጋግጡ በማድረግ፣ እነዚህን ነገሮች (ልዩነቶች) በሚዲያ ምእመኑ እንዲያውቃቸው በማድረግ ምእመናን ልዩነቱ እንዲፈታ የድርሻቸውን እንዲወጡ ማድረግ፡፡

8. ስምምነት ሂደት በመሆኑ፤ ድርድርና ብዙ ጊዜ በማይወስዱ ዋና ዋና በሆኑ ጉዳዮች ላይ ዕርቀ ሰላም ለመፍጠር የሚያስችሉ ግንባር ቀደም የሆኑ ነጥቦችን ለይቶ መስማማት፡፡ ከዚህ በመቀጠልም በአደራዳሪዎች አማካኝነት በቀጣይ ሊታዩ የሚገባቸውን ርእሰ ጉዳዮች ዝርዝርና የሚታዩበትን ሁኔታ አቅጣጫ ማስቀመጥ፡፡
9. በማንኛውም ደረጃ የሚገኙ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን፤ ለዕርቀ ሰላሙ መሳካት እግዚአብሔርን በጸሎት እየጠየቁ፣ አስፈላጊውን ዕገዛና ድጋፍ ማድረግ፡፡ አደራዳሪዎችና ሚዲያዎችም ለሕዝበ ክርስቲያኑ መድረስና መታወቅ ያለበትን መረጃ አስፈላጊነቱን በማየት ሳይዛባ በወቅቱ ተደራሽ እንዲሆን ማድረግ፡፡ አጋዥና ወሳኝነት ያለው ስለሆነ«አባቶች ዕርቀ ሰላምን በመፍጠር፤ ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎትና ለሀገራዊ መግባባት ወሳኝ ሚና ሊጫወቱ ይገባል!» በማለት ማኅበሩ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፤ሐመር  መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁጥር 2 ሰኔ 2010 ዓ.ም

ማኅበረ ካህናት ዘሰሜን አሜሪካ Mahibere Kahinat North America

ማኅበረ ካህናት ዘሰሜን አሜሪካ

ማኅበረ ካህናት ዘሰሜን አሜሪካ

                              ከሁሉ አስቀድመን እኛ የመንፈስ ልጆቻችሁ ካለንበት ከሰሜን አሜሪካ ሆነን ቡራኬአችሁ ይድረሰን እንላለን!

ውድ አባቶቻችን የታላቋ ቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር ላለፉት ከሃያ ዓመታት በላይ ለሁለት መከፈል ምክንያት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የደረሰውን ውድቀት በእኛ በመንፈስ ልጆቻችሁ ካህናት እንዲሁም ምዕመናን ላይ የደረሰውን ሐዘን ታላቅነት ለቤተ ክርስቲያን ከእናንተ በላይ የቀረበ ባለቤት ስለሌላት ከእናንተ በላይ የሚረዳው ሊኖር አይችልም፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በኢትዮጵያ ከመንግሥት ምሥረታ ጀምሮ የነበራትን አስተዋጽዖ፣ እንዲሁም በዕውቀት ምንጭነትና በታሪክ መሠረትነት የነበራት ስፍራ እየደበዘዘ ተቀባይነቷ እየቀነስ፣ እንዲሁም ለአገር ግንባታና ለትውልድ ጥቅም ልታውለው የምትችለው የእናንተ የአባቶቻችን ሊቃውንት ዕውቀትና የእኛ የልጆቿ የካናትና ጸጋ፣ የምዕመናን ልጆቿ የትምህርት ችሎታ፣ ገንዘብና የሰው ኃይል በአንድነት እጦት ባክኗል፤ እየባከነም ይገኛል፡፡ ይህ በመሆኑም ሲቆጫችሁና ሲያንገበግባችሁ እንደኖረም እኛ ካህናት በቅርብ ስለ ምናውቃችሁ ነጋሪ አያሻንም፡፡ ከዚህም የተነሳ እኛ በሰሜን አሜሪካ የምንገኝ ካህናት የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት ለማስመለሰ የበኩላችንን ጥረት ስናደርግ ቆይተናል፡፡

በሀገራችን በኢትዮጵያ ወቅቱ የይቅርታና የመቻቻል ጊዜ እየሆነ ነው፡፡ ይህ ጊዜ ስትጸልዩበት ስታለቅሱበትና ስትናፍቁት የነበረው የኢትዮጵያ ትንሣኤ እየታየ ያለበት ወቅት ነው፡፡ በፖለቲካ አመለካከታቸው ተለያይተውና ተራርቀው በጠላትነት ይፈራረጁና አንዱ ሌላኛውን ሽብርተኛ ይል የነበረበት ሁኔታ ተቀይሮ አንዱ ለአንዱ ምሕረት እያደረገ እየታረቁ ይገኛሉ፡፡ እንዲሁም በብዙ ዐሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ታራሚዎች በመንግሥት ምሕረት እየተፈቱ የሚገኙበት ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ ወቅቱ የጸሎታችሁንም ውጤት በዓይታችሁ እያያችሁ የምትገኙበት ወቅት ነው፡፡ ይህ እየሆነ በሚገኝበት በዚህ ወሳኝ የይቅርታ ወቅት ከይቅርታ መምህራን የሚጠበቀውን ይቅርታ ለታላቋ ቤተ ክርስቲያናችን ተልዕኮ ስትሉ አለመተግበር የእኛን የልጆቻችሁን ልብ ምን ያህል ሊጎዳ እንደሚችልና ይልቁንም አሁን የሚደረገው እርቅ ባይሳካ የቤተ ክርስቲያናችንን ጉዳይ ምን ያህል እንደሚያወሳስበውና አገልግሎታችንንም ምን ያህል እንደሚጎዳው እንድትረዱልን እንወድዳለን፡፡

እኛ የሰሜን አሜሪካ ካህናት እናንተን አባቶቻችንን ወደ ላይ መናገር ሥርዓቱም የክህነቱ የሥነ ምግባር ሕግም እንደ ማይፈቅድልን እንረዳለን፡፡ ይሁን እንጂ ልጅ የጎደለበትን ለማግኘት አባቱን መጠየቅ የልጅነት ወጉ በመሆኑ የልጅነት መብታችንን ተጠቅመን በልጅነታችን እንድትፈጽሙልን የምንሻውን ጥያቄ በልጅነት ፍቅር ስናቀርብ በአባት ፍቅር ተረድታችሁ እንድትመልሱልን በታላቅ አክብሮትና ትሕትና የሚከተሉትን ጥያቄዎቻችንን እናቀርባለን፤

1ኛ. እንደሚታወቀው ሁሉ የኢትዮጵያ መንግሥት በወሰደው ለውጥ እርምጃ በሕግ ሽብርተኛ የተባሉ የፖለቲካ ድርጅቶች ከሽብርተኛ መዝገብ ነጻ በሆኑበት፣ ለ20 ዓመታት በጠላትነት ይፈላለጉ የነበሩ ከ60 ሺህ በላይ ዜጎች ያለቁበት የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦች የጦርነት ታሪክ ተቋጭቶ እርቅ የተፈጸመበት ወቅት ነው፡፡ ስለዚህ አባቶቻችንን የምንጠይቅበት በኢትዮጵያ ከዚህ በፊት ከኢትዮጵያ ውጭ ባለው አስተዳደር ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተላለፈው ውግዘት ለዕርቁ ስኬት ሲባል አስታራቂ አባቶች ወደ ሰሜን አሜሪካ ከመምጣታቸው በፊት እንዲነሳ እንጠይቃለን፡፡ ይህ ሳይሆን ቀርቶ በሰበብ አስባቡ እርቁ ባይሳካ በውጭ ያለው አስተዳደር ኢትዮጵያ ገብቶ ጽ/ቤት ከፍቶ ሥራውን ለመጀመር የሚያዳግተው ምንም ዓይነት የፖለቲካ ተጽዕኖ እንደማይኖር በመንግሥት የተረጋገጠ ስለሆነ ይህን ጥፋት ለማስቀረት ወቅቱ አሁን መሆኑን ለአባቶቻችን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

  2ኛ. እኛ የሰሜን አሜሪካ ማኅበረ ካህናት ቤተ ክርስቲያናችን ከዚህ በፊት የቤተ ክርስቲያን አምላክ እግዚብሔር የስጣትን ዕድል ሳትጠቀምበት የቀረችበት ጊዜ አያሌ በመሆኑ የተሰማን ሐዘን ከፍተኛ ቢሆንም ዳግመኛ ዕድል መስጠት የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ እግዚአብሔር አሁን የሰጣት ዕድል ወሳኝ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያን ይህን ዕድል እንድትጠቀምበት አባቶቻችንን በታላቅ አክብሮት እየጠየቅን ይህ ሳይሆን ቀርቶ እርቁ ሳይሳካ ቢቀር በአንዲት እምነት ሁለት አስተዳደር ምክንያት ከማንኛውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናት በላይ ተጎጂ የሆንነው እኛ የሰሜን አሜሪካ ካህናት በመሆናችን ቤተ ክርስቲያናችንን ለመታደግ ያለ ምንም ልዩነት የአገር ውስጥና የውጭ አስተዳደር ብለን ሳንከፋፈል ለማገልገል የወሰንን መሆናችንን በትሕትና እናስታውቃለን፡፡

ስለዚ ውድ አባቶቻችን ቤተ ክርስቲያናችን የበለጠ ችግር ውስጥ ከመግባቷ በፊት ለቤተ ክርስቲያንና ለአገር የሚበጅ የለውጥ እርምጃ እንድትወስዱ በታላቅ አክብሮት እንጠይቃለን፡፡

ከዚህ ደብዳቤ ጋር የማኅበሩ አባላት የ246 ካህናትን ሥም ዝርዝር አባሪ አድርገን የላክን መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ሰይፈ ገብርኤል አብሰን

የሰሜን አሜሪካ ማኅበረ ካህናት ሰብሳቢ

ግልባጭ፡-

  • ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊት ዲሞክራሲያዊት መንግሥት ጠ/ሚ ጽ/ቤት

 

በቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል ተፈጥሮ የቆየው አለመግባባት እንዲያበቃ ለማድረግ እና ሰላምና አንድነትን ማምጣት እንዲቻል በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሰጠ መግለጫ

               በቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል ተፈጥሮ የቆየው አለመግባባት እንዲያበቃ ለማድረግ እና ሰላምና አንድነትን ማምጣት እንዲቻል በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሰጠ መግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምር ለ2000 ዓመታት አንድነቷን፣ ዶግማዋንና ቀኖናዋን ጠብቃ የቆየች ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በተለያዩ ዘመናት የውጭና የውስጥ ፈተናዎች ቢፈራረቁባትም ፈተናዎቹን በመቋቋም፣ እምነቷን በማጽናት፣ ቀኖናዋንና ትውፊቷን በመጠበቅ፣ ተከታዮቿን በመምከርና በማስተማር ሀገርን ሰላም እያደረገች ኖራለች፡
ሆኖም በ1984 ዓ.ም. የነበሩት 4ኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ መንበራቸውን መልቀቃቸውን ተከትሎ ከተወሰኑ አባቶች ጋር ከአገር በመውጣታቸው ምክንያት በቤተ ክርስቲያናችን ለ26 ዓመታት ተከታዮቿ ምእመናን እያዘኑ በከፍተኛ የሰላም እጦት ውስጥ አሳልፏለች
ይህ ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ የጠፋውን ሰላም ወደነበረበት እንዲመለስ ለማድረግ ከችግሩ መፈጠር መነሻ ማግስት እና ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ ቅዱስ ሲኖዶስ በአራት የተለያዩ የስብሰባ ጊዜያት ዕርቀ ሰላሙን ለማምጣት ሊቃነ ጳጳሳትን መድቦ አሜሪካ ድረስ በመላክ ከፍተኛ ጥረት አድርጓል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜያት በሚያደርጋቸው ጉባኤያት የሰላሙ በር ክፍት መሆኑን በመግለጽ የሰላም ጥሪ ሲያስተላልፍ ቆይቷል፡፡
ይህ የምእመናን ልጆቻችን የሰላም ጥማትና የዘወትር ጸሎት የቅዱስ ሲኖዶስ የዕለት ከዕለት የሰላም ጥረት ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶ ሰላሙ መቋጫ ወደሚያገኝበት ደረጃ እንዲደርስ የ2010 የጥቅምት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤን ተከትሎ በራሱ ተነሳሽነት ከካህናትና ምእመናን የተውጣጣ የሰላም ኮሚቴ ያቀረበውን የዕርቀ ሰላም ጥያቄ በአዎንታ ተቀብሎት ቀደም ሲል ተጀምሮ የነበረው የዕርቅ ሰላም ሂደት ተጠናክሮ እንዲቀጥልና የመጨረሻ እልባት እንዲያገኝ ሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ሰይሟል፡፡
በዚሁ መሠረት ከሐምሌ 11 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ በአባቶች መካከል የሚካሄደው የዕርቀ ሰላም ሂደት ፍጻሜ የሚያገኝበት በውጭ አገር የሚገኙ አባቶች ወደ አገር ቤት የሚገቡበት ፍጹም የቤተ ክርስቲያናችን አንድነት የሚመለስበት እንዲሆን በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት ካህናትና ምእመናን በጸሎት እንድትተጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡
አገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ በአዲስ መንፈስ እየሄደችበት ያለው የሕዝቡን ሰላምና አንድነት ማረጋገጥ ውጤታማ እየሆነ መጥቷል፡፡
ከዚሁ ጋር ለዘመናት አንድነትና ቤተሰባዊነት የነበራቸው የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዘቦች ወደ ፍጹም ሰላም እንዲመጡ እየተከናወነ ያለው ጅምር ቤተ ክርስቲያናችን በእጅጉ የምትደግፈውና ለመጨረሻውም ግብ የበኩሏን አስተዋጽኦ የምታደርግበት ይሆናል፡፡
ቤተ ክርስቲያናችን በአሁኑ ጊዜ በውስጧ የሚገኙ ችግሮቿን ከጥንት ጀምሮ ይዛው በቆየችው ትዕግሥትና የሰላም ሂደት በቀኖናዋ ወሠረት የምትፈታው ሲሆን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቷን በብቃት የምታከናውንበት አቅጣጫ ቅዱስ ሲኖዶስ አስቀምጧል፡፡
በቀጣይ ወቅቱንና ዘመኑን በዋጀ መልኩ መልካም አስተዳደርን በቤተ ክርስቲያናችን ካለፈው በበለጠ ማስፈን እንዲቻል የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግሮች ሊፈቃ ያስችላል በሚል በባለሙያዎች የተዘጋጀውን መሪ ዕቅድና ከአሁን በፊት የተጠኑ ጥናቶች በተግባር ማዋል እንዲቻል ጥናቶቹ ለ2011 ዓ.ም. የጥቅምቱ ምልዓተ ጉባኤ ዋና የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ እንዲቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
አሁን በቤተ ክርስቲያናችን አባቶች መካከል የተጀመረው ዕርቀ ሰላም ያለምንም መሰናከል ለውጤት ይበቃ ዘንድ ዕርቀ ሰላሙን አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ ከሰጠው አካል በስተቀር መግለጫ መስጠት ጠቃሚ አለመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ አበክሮ ያሳስባል፡፡
በዕርቀ ሰላሙ ሂደት በሚደረገው ማንኛውም ውይይት የነበረውንና ቤተ ክርቲያናችን ይዛው የቆየችው ቀኖና በተመለከተ ውይይቱም ሆነ ዕይታው በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መሠረት በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ብቻ የሚታይ ይሆናል፡፡
አሁን ለተጀመረው የዕርቀ ሰላምና የአንድነት መገኘት የቅዱስ ሲኖዶሱን ውክልና ይዘው ወደ አሜሪካ የሚጓዙ ብፁዓን አባቶች ጉዞአቸው የተቃናና የተሳካ ሆኖ ችግሩ የመጨረሻ እልባት እንዲያገኝ ሁላችንም ተባብረን እንድንሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ለአገራችንና
ለሕዝባችን ሰላሙን ይስጥልን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ
ሐምሌ 4 ቀን 2010 ዓ.ም
አዲስ አበባ

«ጸልዩ በእንተ ሰላም፤ስለ ሰላም ጸልዩ» (ሥርዓተ ቅዳሴ)

ሐመር  መጽሔት   26ኛ ዓመት ቊጥር 2፤ ሰኔ 2010 ዓ.ም

                                                                                                                                              በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

ዓለም የሚሻት፤እርሷም ለዓለም የምታስፈልገው አንዲት ነገር አለች፡፡ያለ እርሷ በዓለም መኖር አይቻልም፡፡ በዓለም መኖር ብቻም ሳይሆን ሰማያዊ ርስትን መውረስም አይቻልም፡፡ስለ ሰላም ሲነገር ቃሉ ይጣፍጣል፤ ስለ ሰላም ሲሰማ ዕዝነ ልቡና ይረካል ሰላም  የተቅበዘበዙትን ታረጋጋለች፤ያዘኑትን ታስደስታለች፤ ጦርነትን ወደ ፍቅር ትለውጣለች፡፡ሰላም በፍለጋ ብቻ የምትገኝ ሳትሆን በተግባር የምትተረጎም ናትና በሰላም የኖሩት ሰላምን በተግባር ያረጋገጡ ብቻ ናቸው፡፡ ምክንቱም ሰላም ተግባራዊ ናትና፡፡ሰላምን በተግባር ለማዋል ደግሞ ሰላምን መሻት ቅድሚያ የሚሰጠው ነው፡፡«ለምኑ ይሰጣችሁማል፤ፈልጉ ታገኙማላችሁ»እንዲል(ማቴ.7÷7፣ ሉቃ. 11÷9) ስለ ሰላም ምሁራን ጽፈዋል፤ ተርጓምያን አመሥጥረዋል፤ ባለ ቅኔዎች ቅኔ ተቀኝተዋል፤ የመዝገበ ቃላት ምሁራን ብያኔ ሰጥተዋል፡፡

ለአብነትም ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላቸው ላይ ሰላም ማለት«ፍጹም፣ ጤና፣ ዕረፍት፣ ዕርቅ፣ ፍቅር፣ አንድነት፣ ደኅንነት፣ ተድላ፣ ገጽታ፣ሰላምታ፣ የቡራኬ የምርቃት ቃል፣ ሰው ሲገናኝ ሲለያይ የሚለው የሚናገረው ወይም የሚጽፈው ማለት ነው» ብለው ቃላዊ ትርጉሙን አስቀምጠውታል፡፡ (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ገጽ-888)

ከላይ በተዘረዘረው የመዝገበ ቃላት ትርጉም መሠረት ሰላም ማለት ሁሉም ነገር ነው፡፡ሰላም ያለው ሰው ፍቅር አለው፤ሰላም ያለው ሰው ዕረፍት አለው፤ጤና አለው፤ ደኅንነት አለው፡፡ ሰላም ያለው ሰው ሁሉም ነገር አለው፡፡ ከላይ የተዘረዘሩትን የሕይወት ቁልፍ ነገሮች ማግኘት የሚቻለው በሰላም ነው፡፡ ሰላም ከሌለ ደግሞ እነዚህ ነገሮች ሁሉ አይገኙም፡፡እነዚህ የሕይወት ቁልፍ ነገሮች ከሌሉም ጽድቅ ትሩፋት አንድነት አይኖርም፡፡ከላይ የተዘረዘሩትን ነገሮች ለማግኘት ሰላምን መሻት፣በሰላም መኖር ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም ነው«ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ» በማለት ቅዱስ ጳውሎስ የሚያስተምረን (ሮሜ12÷18) በሰላም መኖር ካልቻልን ሕይወታችን የክርስቶስን መስቀል ተሸክሟል ለማለት እንቸገራለንና የሐዋርያው ቃል እውነት አለው፡፡የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት እንደሚያስረዳን የሰው ልጅ ሲኖር ከእገሌና ከእገሌ ጋር ብቻ ብሎ ሳይሆን ከማንኛውም ሰው ጋር በሰላም መኖር ክርስቲያናዊ መገለጫው፣ክርስቲናዊ ሥነ ምግባሩ ነው፡፡ሰላም ውስጣዊና ውጫዊ እንደመሆኑ፣ውስጣዊ ሰላምን የምናገኘውም ከላይ ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም መኖር ስንችል ብቻ ነው፡፡ከሰው ጋር ሰላም ከሌለን ሰላማችንን የምናጣው ከሰዎች ጋር ባለን ማኅበራዊ ግንኙነት ብቻ አይደለም፤ከልደታችን እስከ ሞታችን ድረስ አብሮን በሚኖረው ማንነታችንም ውስጥ ነው፡፡ ከሰው ጋር ብቻ ሳይሆን ከራሱ ጋር ተጣልቶ የሚባዝን፣ለራሱ ሰላምን የነሣ ብዙ ሰው አለና ሰላምን መሻት፣ ሰላማዊ መሆን ከራስ ጋር በመታረቅ ይጀመራል፡፡

አባቶቻችን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም ሆኑ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያን እየመሩ የቆዩ ታላላቅ የሀገር መሪዎች ሃይማኖትን ጠብቀው፣ዳር ድንበርን አስከብረው፣ሃይማኖትንና ሀገርን ከዚህ ማድረስ የቻሉት በሰላም ነው፡፡ያለ ሰላም ዛሬን ውሎ ነገን መድገም አይቻልም፡፡በሰላም ግን ትናንትን ማስታወስ፣ዛሬን ማስተዋል፣ነገን ደግሞ ተስፋ ማድረግ ይቻላል፡፡ሰላም ባለበት ሞት የለም፤ሰላም በሌለበት ግን ውድቀት አለ፡፡ሰላም ያለው ለሚሠራው ለሚያደርገው ለሚኖረው ሁሉ ድፍረት አለው፤ሰላም የሌለው ሰው በፍርሀት ወጀብ ሲናወጥ ይኖራል፡፡ ለዚህም ነው በሰላም ያለ ሰው መፍራትና ሞት እንደሌለበት ቅዱስ መጽሐፍ የተናገረው፡፡ (መሳ.6÷23)

 ከሰላም የምናገኘው ጥቅም ምድራዊ ብቻ እንዳልሆነም ቅዱስ መጽሐፍ ያስረዳናል፡፡ሰማያዊ ርስታችን ገነት መንግሥተ ሰማያት የምንወርሰው በሰላም ነው፡፡ሰላም ያለው ሰው ጽድቅን ይሠራል፡፡ጽድቅን የሚሠራም ሰላም አለው፡፡ሰላም ያለው ሰው ለድሆች ይራራል፤ለድሆች የሚራራም ሰላም አለው፡፡ ሰላም ያለው ሰው በማቴ 25 ላይ እንደተጠቀሰው ለተራበ ያበላል፤ ለተጠማ ያጠጣል፤ ለታረዘ ያለብሳል፤ የታሠረ ይጠይቃል፡፡ በዚህም ሥራው በትንሣኤ ዘጉባኤ ትንሣኤ ዘለክብርን ያገኛል፡፡ሰላም የሌለው ሰው ደግሞ በተራበ ይጨክናል፤ ለተጠማ አያዝንም፤ የታመመ አይጠይቅም፤የታረዘ አያለብስም፤በዚህም ምክንያት በትንሣኤ ዘጉባኤ ትንሣኤ ዘለኀሣርን ያገኛል፡፡(ማቴ35÷42) ከዚህ ላይ እንደምንረዳው ሰላም የብፅዕና የጽድቅ መንገድ መሆኗን ነው፡፡ለዚህም ነው«ብፁዓን ገባርያነ ሰላም፤ሰላምን ዕርቅን የሚያደርጉ ብፁዓን ናቸው» ተብሎ ሰላምን ዕርቅን ማድረግ ብፅዕና መሆኑ የተገለጠልን (ማቴ.5÷9)

በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን አውታሮች እንደምንገነዘበው በተለያዩ ጊዜያት ዓለም በሰላም እጦት ስትናጥ ቆይታለች፡፡በዚህም የተነሣ ብዙ ሰው ሠራሽ ንብረቶች ከማለቃቸው በተጨማሪ እጅግ ክቡሩና በአምሳለ እግዚአብሔር የተፈጠረው የሰው ልጅ እንደ ተራ ነገር በየሜዳው ወድቆ ቀርቷል፡፡ለዚህም በአንደኛውና በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በዓለማችን ላይ የደረሰው ኪሳራ ማሳያ ነው፡፡በሀገራችንም በተለያዩ ጊዜያት በሥልጣን፣በሃይማኖትና በተለያዩ ምክንያቶች ብዙ የሰው ሕይወት ተቀጥፏል፡፡ በጣሊያን ጦርነት፣በእንግሊዝ ወረራ፣በግራኝ አሕመድ ሃይማኖታዊ ጥቃት፣ በዮዲት ጉዲት ዐመፅ በርካታ የሰው ልጅ ተቀጥፏል፤በሰላም ተከፍተው የነበሩ በሮች በሞት ተዘግተዋል፡፡ምድራችን በደም ታጥባለች፣አረጋውያን ያለ ጧሪ ቀባሪ ቀርተዋል፤ሕፃናት ያለ አሳዳጊ ብቻቸውን ሆነዋል፡፡ 

በየቤታችን በየጓዳችን ስንመለከት እንኳን ተኳርፎ፣ተበጣብጦ፣ፍቅርን አጥቶ የሚያድረው ብዙ ነው፡፡ይህ ሁሉ አለመረጋጋትና መባዘን የሚመጣው በሰላም ማጣት ብቻ ነው፡፡ያለ ሰላም መኖር እንቅልፍ መተኛት እንኳን አይቻልም፡፡ሰላም ያለው ሰው ግን በእግዚአብሔር ተባርኮ ሰላም እንቅልፍ መተኛት ይችላል፤ በሰላም ወጥቶ በሰላም ይገባል፡፡የሰው ልጅ በእምነት ኖሮ፣ ሠርቶ የሚገባው፣አንቀላፍቶ የሚነሣው ሰላም ሲኖረው ብቻ ነው፡፡«በሰላም እተኛለሁ አንቀላፋለሁም፤አቤቱ አንተ ብቻህን በእምነት አሳድረኸኛልና» እንዲል (መዝ 4÷8)

ፍቅር በሰው ልጆች እንዲሠርጽ፣ መግባባት እንዲኖር፣መረዳዳትና መከባበር እንዲመጣ በመንፈሳዊ ተቋማት በሓላፊነት የሚገኙ ሰዎች ሰላምን ማስተማር አለባቸው፡፡መሪዎች የሰላም አክባሪ ሲሆኑ ተመሪው ሕዝብ ሰላምን ይከተላል፡፡የሃይማኖትና የቤተ እምነቶች መሪዎችና አባቶች የሰላም ሰባኪ ሲሆኑ ምእመናን(የእያንዳንዱ ቤተ እምነት ተከታይ)የሰላም ባለቤት ይሆናሉ፡፡ተመሪ ሁልጊዜም ቢሆን መሪውን ያያል፡፡ ሰላማዊ መሪ እንደ ሙሴ ባሕር ከፍሎ ሕዝቡን ያሻግራል፡፡ሰላም የሌለው መሪ ደግሞ እንደ ፈርዖን እስከ ሠራዊቱ ይሰጥማል፡፡ሕፃን የእናት የአባቱን የታላላቆቹን አርአያ ይዞ እንደሚያድግ ሕዝብም መሪዎቹን፣አባቶቹን ይከተላል፡፡የሃይማኖት አባቶች የሰላም ሰባኪ ሳይሆኑ ሰላማዊ ምእመናንን አፍርቶ ማለፍ ቀላል አይደለም፡፡ የተከፋፈለ መሪ የተከፋፈለ ሕዝብን ያፈራልና፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ሁልጊዜም ቢሆን «ጸልዩ በእንተ ሰላም፤ስለ ሰላም ጸልዩ» እያለች ለሁሉም ሰላም እንደሚያስፈልግ ከሰበከች በኋላ፣ለቅድስት ቤተ ክርስቲንም ሰላም እንደሚሻት ስታስተምር«ጸልዩ በእንተ ሰላመ ቤተ ክርስቲያን ስለ ቤተ ክርስቲያን ሰላም ጸልዩ» እያለች ልጆቿን ትመክራለች (ሥርዓተ ቅዳሴ) ይሁን እንጂ በሰላም ማጣት ምክንያት እንደ እናት ቤተ ክርስቲያን የችግር ገፈት ስንቀምስ መቆየታችን የቅርብ ጊዜ ትዝታ ብቻ ሳይሆን አሁን ያለው እውነታ ነው፡፡

ሰላምን የምታስተምር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ኵላዊት ናትና ለዓለም ሁሉ የሰላም አርአያ ልትሆን እንደሚገባ ሁሉንም አካል የሚያስማማ ነው፡፡የቤተ ክርስቲያን ሰላም የሚታየው ደግሞ በእኛ በልጆቿ ነው፡፡ነገር ግን በውስጣዊም ይሁን በውጫዊ ምክንያት የእኛ የልጆቿ ሰላም ሲደፍርስ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሰላም ይደፈርሳል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲናችን ሓላፊነትን የሰጠቻቸው ብፁዓን አበው በጸሎታቸው ለቅድስት ቤተ ክርስቲንና ለሀገር፣በአስተዳደራቸውና በትህርምትነታቸው ደግሞ ለእኛ ለልጆቻቸው አርአያ የሚሆኑን፣ቡራኬን የሚሰጡን የምንባረክባቸው የእግዚአብሔር ስጦታዎቻችን ናቸው፡፡

እግዚአብሔር እነርሱን የሰጠንም ፈጥሮ ስለማይተወን፣እንድንበዛ መንግሥቱን እንድንወርስ፣ እንዳንጠፋ፣እንዳንናወጽ፣እንድንረጋጋ፣በሰላም እንድንኖር፣ በመጨረሻም መንግሥቱን እንድንወርስ ስለሚፈልግ ነው፡፡«ኢየኀድጋ ለሀገር ዘእንበለ አሐዱ ሔር፤ያለ አንዳች ቸር ደግ አስተማሪ ሰው ሀገርን እንዲሁ አይተዋትም»እንዲል መጽሐፍ፡፡ከዚህ በተጨማሪም ለምድራችንና ለሕዝባችን አባቶቻችን እንደሚያስፈልጉን«ኢኀደጋ ለምድር እምቅድመ ዓለም ወእስከ ለዓለም ዘእንበለ ካህናት ወዲያቆናት፤ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስከ መጨረሻው ድረስ ምድርን ያለ ካህናትና ዲያቆናት አይተዋትም»በማለት ይናገራል (ኅዳር ጽዮን ዋዜማ) ይሁን እንጂ ኢየሱስ ክርስቶስን በገዳመ ቆሮንቶስ በሦስቱ አርእስተ ኃጣውእ ለመፈተን ኀፍረት ያልተሰማው ጠላት ዲያብሎስ አባቶቻችንንም የተለያዩ ምክንያቶችን መሠረት በማድረግ ለመፈተን ሞክሯል፡በመረጃ የተወገዙ መናፍቃንም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንደ መጠለያ በመጠቀም  ሕዝቡን አውከዋል፤ ቤተ ክርስቲያንንም እየበጠበጡ ይገኛሉ፡፡

በተለያዩ ጊዜያት አባቶቻችንን አንድ ለማድረግና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንንም ከመከፋፈል ለመታደግ በተደረገው ጥረት እንኳን ድብቅ ዓላማቸው እንዳይሰናከል ለማድረግ የዕርቁን ሂደት ሲያሰናክሉ መቆየታቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ለእነርሱ የዓላማ መሳካትም ሆነ ለምእመናን መበታተን የዕርቀ ሰላሙ አለመሳካት ወሳኝ ነውና በሁለቱም (በሀገር ውስጥም  በውጭም)  በሚገኙ መካከል  ዕርቀ ሰላሙን የማይደግፉ አካላት መኖራቸው የማይካድ ነው፡፡የእነዚህን አካላት ዓላማ ተረድቶ ቅድሚያ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ልዕልና መቆም ከብፁዓን አበው ጀምሮ የእያንዳንዳችን ምእመናን ድርሻ ነው፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በቅዳሴዋ በወንጌሏ፣ በእያንዳንዱ የወንበር ትምህርቷ ሰላምን ታስተምራለች፤ልጆቿን«ጸልዩ በእንተ ሰላመ ቤተ ክርስቲያን አሐቲ ቅድስት ጉባኤ እንተ ሐዋርያት ርትዕት በኀበ እግዚአብሔር፤ የሐዋርያት  ጉባኤ ስለሆነችው በእግዚአብሔር ዘንድም ርትዕት ስለሆነችው አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጸልዩ» እያለች ማስተማሯ ማዘዟ ለሰላም ያላትን አቋም ያመለክታል (ሥርዓተ ቅዳሴ) ስለ ቤተ ክርስቲያን ሰላም መጸለይ ስለ ምእመናን ስለ ሕዝብ መጸለይ ነው፡፡ስለ ሕዝብ መጸለይ ደግሞ ስለ ሀገር መጸለይ ነው፡፡የቤተ ክርስቲያንን ሰላም መሻት የአንድን ምእመን ሰላም መሻት ነው፤ቤተ ክርስቲያን ማለት የምእመናን ኅብረትና እያንዳንዱን አማኝ የሚመለከት ነውና፡፡ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሁሉም ድኅነትና ሰላም የምትጸልየው፡፡ሌላው ይቅርና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለ እናት ሀገራቸው ሲሉ በየበረሃው ያሉ ሀገር ጠባቂዎችን የማትዘነጋ ርኅሩኅ እናት ናት፡፡ለዚህም ነው«ዕቀብ ሕዝባ ወሠራዊታ ለሀገሪትነ ኢትዮጵያ፤የኢትዮጵያ ሀገራችንን ሕዝቦቿንና ሠራዊቷን ጠብቅላት» እያለች በዘወትር የቅዳሴ ሥርዓቷ የምትጸልየው፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ቅድስት ቤተ ክርስቲንን በደሙ ሲመሠርታት ጠብን ጥልን ክርክርን በሞቱ ገድሎ፣በደሙ አንጽቶ ነው፡፡ይህ ለዓለም ሰላም የተከፈለ ዋጋ፣ለድኅነታችን የተሰጠ ሥጦታ፣ ለሰላም የተጠራንበት መንገድ ነው፡፡ አይሁድ ክርስቶስን በጥላቻ ቢሰቅሉትም እርሱ ግን የተሰቀለው ለሰላም ነው፡፡አይሁድ ክርስቶስን በጥላቻ ቢገርፉትም እርሱ ግን በትሕትና የተገረፈው ሰላምን ለማምጣት ነው፡፡የተቅበዘበዘው፣ሰላም ያጣው፣በሞት ጥላ ሥር የነበረው ዓለም፤መዳንንና ሰላምን የሚያገኘው በክርስቶስ ሞት በክርስቶስ መስቀል ነበርና፡፡ለዚህም ነው የቤተ ክርስቲያን ብርሃን የሆነው ቅዱስ ያሬድ«ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፤በመስቀሉ ሰላምን አደረገ» በማለት የተናገረው (መጽሐፈ ድጓ)

ይህ ሁሉ ዋጋ የተከፈለለትን ሰላም በተግባር አለመኖር ዋጋ ያስከፍላል፡፡ በክርስቶስ ሞት የተሰጠንን ሰላም በከንቱ መጣል የክርስቶስን ዋጋ እንደ ማቃለል ይቆጠራል፡፡ ክርስቶስ በመስቀሉ ለዓለም የሰጠውን ሰላም ገንዘብ አለማድረግ የመስቀሉን ስጦታ አለመቀበል ነው፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጠው የተጠራነው በፍቅር በሰላም ልንኖር ነውና ሰላም ገንዘባችን ሊሆን ይገባል (1ኛቆሮ7÷15)

«ወንድሞች ሆይ በመካከላችሁ የሚደክሙትን በጌታም የሚገዟችሁን የሚገሥጿችሁንም ታውቁ ዘንድ ስለ ሥራቸውም በፍቅር ከመጠን ይልቅ ታከብሯቸው ዘንድ እንለምናችኋለን፡፡ እርስ በርሳችሁ በሰላም ኑሩ»እንዳለው ሰዎችን በሥራቸው እያከበርን፣ ግሣጼንና ምክርን እየተቀበልን፣ከጥፋታችን እየታረምን በሰላምና በፍቅር መኖር ይጠበቅብናል(1ኛተሰ.5÷12) ይህንን ስናደርግ በሰላም መኖራችን ዕረፍት ያሳጣቸው አካላት ቢኖሩ እንኳን እኛ የሰላምን ጥሪ ማዳመጥ፣ የሰላምን ደወል መስማት፣መንገዷንም መከተል ይገባናል፡፡ይህ ሲሆን ነው ራሳችን ወድደን ዓለምንም በፍቅር ልናሸንፍ የምንችለው፡፡

በሰላም የማይኖር ሰው ዓለምን ማሸነፉ ይቅርና አባቱን ሊያከብር እናቱንም ሊወድ አይችልም፡፡ ሰላም የሌለው ሰው ወንድሙን ሊወድ  እኅቱንም ሊያስደስት አይችልም፡፡ ሰላም የሌለው ሰው ቤተሰብ መሥርቶ ሊያስተዳድር፣ ሀገርንም ሊመራ አይችልም፡፡ሌላው ይቅርና ሰላም የሌለው ሰው ራሱን ይወድ ዘንድ ከራሱ ጋርም በሰላም ይኖር ዘንድ አይቻለውም፡፡ሰላም የፍቅር እናት፣ የአብሮነት ምሰሶ፣የጽድቅ መንገድ፣ የመከባበር ምዕራፍ ናትና፡፡

በመሆኑም ከሕፃን እስከ ዐዋቂ፣ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ ከመምህሩ እስከ ደቀ መዝሙሩ ስለ ሰላም ማሰብ ማስተማርና መኖርን ገንዘብ ማድረግ ይገባል፡፡ቤተ ክርስቲያንን እንዲመሩ ሥልጣኑን ከእግዚአብሔር የተረከቡ አበው፣ካህናት፣ዲያቆናትም ሰላምን ለምእመናን እየሰበኩ እያስተማሩ፣ በሰላም መኖርን ለሚሻው ሕዝባቸው ሰላምን ማብሠር አለባቸው፡፡ባለፉት ጊዜያት በጠላት ዲያብሎስ ሴራ የነበረውና ብዙዎቻችንን አንገት ያስደፋው ሰላም ማጣት ሊጠፋ የሚችለው ሰላምን በተግባር በመተርጎም ብቻ ነውና ይቅር መባባል፣ጥፋትን ማመን፣ባለፈው ጥፋት መጸጸት፣ስለ ቀጣዩ ሰላም ማሰብ፣ አንድነትን መናፈቅ፣ስለ አንድነት መቆም፣የቤተ ክርስቲያንን ልዕልና መጠበቅ ይገባል፡፡ ይህ የሰላም ጉዳይም ለእገሌ ብቻ ተብሎ የሚተው ሳይሆን በተለያዩ አካላትና መዋቅሮች ከሚገኙ ሰዎች ሁሉ የሚጠበቅና ሊተገበር የሚገባው ነው፡፡

    ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሰላም እመቤት የሰላም ተምሳሌት ናት፡፡የራሷን ሰላም አስከብራ ለሌሎችም አርአያ በመሆን ዘመናትን አሳልፋለች፡፡ነገር ግን ዘመናትን ባሳለፈች ቊጥር በሰላም ፈላጊነቷ የማይደሰተው ጠላት ዲያብሎስ ሁልጊዜም ቢሆን ሰላሟን ለመንሳት ተኝቶ አያውቅም «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዘመኑ የተለያዩ ፈተናዎች የተፈራረቁባት ሲሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ናትና የመጣውን የፈተና ጎርፍና ነፋስ ሁሉ ተቋቁማ  አሁን ላለንበት ዘመን ደርሳለች፡፡ የዐላውያን ገዥዎችን ሰይፍ፤ ከውስጥም ከውጭም የነበሩ መናፍቃንን ቅሰጣ ተሻግራ እስከ አሁን የሐዋርያት፣የቅዱሳን ሊቃውንትን የአትናቴዎስን ፣የቄርሎስን ሃይማኖት ይዛ ተገኝታለች» ተብሎ የተጻፈውም ለዚህ ነው (ሐመር 25ኛ ዓመት ቊጥር5) ይህ የሚያሳየው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በተለያዩ የፈተና ወጀቦች ስትታመስ ብትኖርም የሰላም መርከብ ናትና አለመውደቋን ነው፡፡

እንደሚታወቀው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ሥር ሆና ለበርካታ ዓመታት የራሷ መንበረ ፓትርያርክ ሳይኖራት፣የራሷን ፓትርያርክ፣የራሷን ኤጲስ ቆጶሳት ሳትሾም ቆይታለች፡፡ነገር ግን ከአንድ ሺህ ስድስት መቶ ዓመታት በኋላ በአባቶቻችን ጥረት ፈቃደ እግዚአብሔር ተጨምሮበት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የራሷን መንበረ ፓትርያርክ አቋቁማ የራሷን ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ መርጣ፣ ከራሷ ልጆች ኤጲስ ቆጶሳትን ሾማ መገልገል ጀመረች፡፡ይሁን እንጂ፣በ1983 ዓ.ም የገጠማት የመከፋፈል አደጋ ለአገልግሎቷ እጅግ እንቅፋት ሆኖ ቆይቷል፡

  ይህ መከፋፈል አገልግሎቱን በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ለማዳረስ ትልቅ እንቅፋት የሆነ ከመሆኑም ባሻገር የቤተ ክርስቲያንን ተሰሚነትም እጅግ የተፈታተነ ነበር፡፡ከዚህም አልፎ በካህናትና በካህናት መካከል፣እንዲሁም በምእመናን መካከል አለመግባባትን፣ጥላቻን ፈጥሯል፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍ በተለያዩ ጊዜያት ለቤተ ክርስቲያን ሰላም የሚቆረቆሩ አካላት ዕርቅ ለመፍጠርና አንድ ለማድረግ ቢጥሩም፣የቤተ ክርስቲያንን አንድነት የማይፈልጉ አካላት ለእነዚህ ዕርቅ ፈላጊዎች ከግብራቸው ጋር የማይስማማ ስም በመስጠት፣በማሸማቀቅ፣ጉዳዩን ከፖለቲካ ጋር በማያያዝ የታሰበው እንዳይሳካ ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡

አሁን ደግሞ እንደ እግዚብሔር ፈቃድ በአባቶች  ይሁኝታን አግኝቶ የተቋቋመው የሰላምና የአንድነት ጉባኤ ሥራውን በአግባቡ እየተወጣ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡በሀገር ውስጥም በውጭም በሚኖሩ አባቶች መካከልም ጥሩ ተቀባይነትና ፍላጎት እንዳገኘም«…ከአንድ ዓመት በላይ ባደረገው ጥረት ከወትሮው በተለየ ሁኔታ በኹለቱም ወገን አባቶች ዘንድ ለዕርቁ ተፈጻሚነት ከፍተኛ መነሣሣትና አበረታች ምላሽ እየታየ ሲኾን ሒደቱም በጥሩ ኹኔታ ላይ ይገኛል»በማለት በመግለጫው ላይ አሳውቋል (የሰላምና የአንድነት ጉባኤው መግለጫ ሰኔ 1 ቀን፣2010 ዓ.ም)

ይህ ሒደት የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለሚናፍቁ ሰዎች እጅግ የሚያስደስትና ተስፋ ሰጭም ነው፡፡ይሁን እንጂ አሁንም ቢሆን ይህ ዕርቅና ሰላም የማያስደስታቸው አካላት መኖራቸውን መዘንጋት ሞኝነት ነው፡፡ በተቃራኒው ቆመው ዕርቁን ለማደናቀፍ ደፋ ቀና የሚሉ አካላት በውስጥም በውጭም መኖራቸው እሙን ነውና ይህ መልካም ጅምር ከፍጻሜ እንዲደርስ የሁላችንም ጸሎትና ልመና ያስፈልጋል፡፡በውስጥም በውጭም ላሉ አባቶቻችን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያላቸው ቅንነትና ተቆርቋሪነት የማይካድ ሐቅ ቢሆንም፣ይህንን ተቆርቋሪነታቸውን ደግሞ በዕርቅና በአንድነት እንዲያጠነክሩት የሁሉም ምእመናን ፍላጎትና ምኞት ነው፡፡

ዕርቁንና ሰላሙን በጉጉት እየጠበቀ ያለው ሕዝበ ክርስቲያን ስጋቱም በዚያው ልክ ነውና ሰርጎ ገቦች ገብተው እንዳይበጠብጡ ከሁለቱም ወገን ጥንቃቄን ይሻል፡፡ ይህ ስጋት የሕዝበ ክርስቲያኑ ብቻ ሳይሆን ዕርቀ ሰላሙን እያካሄደ ባለው አካልም ያለ እውነታ ነው፡፡ የሰላምና የአንድነት ጉባኤውም «በሁለቱም ወገን ያላችሁ አባቶች የዕርቀ ሰላሙን ሒደት በተመለከተ የምትሰጡት መግለጫ ሓላፊነት በተሞላበትና በጥንቃቄ እንዲኾን አበክረን እንማጸናለን፡፡ ምክንያቱም የተለያዩ አካላት ቃላትን በቅንነት ከማየት ይልቅ ከጭብጡ ውጭ በመተርጎም የተዛባ አመለካከት እንዲፈጠር ማድረግ ላይ የሚያተኩሩ ስለሆነ የቃላት አገላለጹ በራሱ ለድርድሩ እንቅፋት እንዳይሆን በመስጋት ነው»በማለት አባቶች እጅግ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ተማጽኗል (የሰላምና የአንድነት ጉባኤው መግለጫ፣ሰኔ 1፣ 2010 ዓ.ም)

በመሆኑም ብፁዓን አበው የማንንም ወገን የመከፋፈል ሥራ ወደ ጎን ትተው ለዕርቁ ቅድሚያ በመስጠት ቤተ ክርስቲንንና ልጆቻቸውን አንድ ማድረግ፣ምእመናን በጉጉት የሚጠብቁትን ዕርቅ በተግባር ማሳየት፣የጠላት ዲያብሎስን የጥፋት ወጥመድ መሰባበርና ለቆሙላት ቤተ ክርስቲያን ቀኝ እጅ በመሆን ፍጻሜውን እንዲያሳዩን ምኞታችን ነው!

በሁለቱም ወገን የምንገኝ ምእመናንም ዓላማችን አንድ ብቻ እንደሆነ መዘንጋት የለብንም፡፡ የክርስቲያን ዓላማው ሁከትና ብጥብጥ፣ምድራዊ ድሎትና ምድራዊ ምቾት አይደለም፡፡ ሁላችንንም አንድ የምታደርገን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ደግሞ የተመሠረተችው በክርስቶስ ደም ነው፡፡የምታስተምረንም ዘለዓለማዊ መንግሥትን እንጂ ይህንን ኀላፊውን ዓለም እንድንወርስ አይደለም፡፡በመሆኑም የሁላችንም ዓላማ ሰማያዊ መንግሥትን ወርሰን መኖር መሆኑን ለአፍታ እንኳን መዘንጋት የለብንም፡፡

በትንሣኤ ዘጉባኤም የምንጠየቀው ምን ሠራችሁ እንጂ የማን ደጋፊ ነበራችሁ የሚል አይደለም፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ልኮ በደሙ አንድ አድርጎናልና እግዚአብሔር ለሰጠን አንድነት መቆም መጽናት አለብን፡፡ለአባቶቻችን ቅርበት ያለን አካላትም ለዕርቁ እንቅፋት ከመሆን ይልቅ በታየንና በተገለጸልን መጠን ከአባቶቻችን እግር ሥር ቁጭ ብለን መልካሙን መንገድ መጠቆም ይጠበቅብናል፡፡ዛሬ መሠረት የምንጥልለት አንድነት ለልጆቻችን ሕይወትና ለነገዋ ቤተ ክርስቲያን ጥንካሬ ወሳኝ ነው፡፡በመሆኑም በማወቅም ሆነ ባለማወቅ የክፍፍሉ ቀጥተኛም ሆነ ኢ-ቀጥተኛ ተሳታፊ የሆን ምእመናን ሁሉ ያለፈው ይበቃል ብለን አንድነቱ እንዲፈጠር በሐሳብ፣በጸሎት ልንተጋ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

                                                        ምንጭ፤ሐመር  መጽሔት 26ኛ ዓመት ቊጥር 2፤ ሰኔ 2010 ዓ.ም

 

ከመገልገያው አገልጋዩ መቅደም እንዳለበት ተነገረ

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስና ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ

                                                                                                                                                                 በካሳሁን ለምለሙ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መቄት ወረዳ አሰፋ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የተገነባው የአብነት ትምህርት ቤት ሕንፃ ሚያዝያ ፳፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በተመረቀበት ወቅት ከመገልገያው አገልጋዩ መቅደም እንዳለበት የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ ተናገሩ፡፡
እንደ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ ገለፃ አብነት ትምህርት ቤቶች የቤተ ክርስቲያን የዕውቀት ማእከል በመሆናቸው ከተዳከሙ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ሊኖር የማይችል መሆኑን ገልጠዋል፡፡ አብነት ትምህርት ቤቶች ትኩረት ከተሰጣቸውና ዘመኑን የዋጁ ካህናት ማውጣት ከተቻለ የቤተ ክርስቲያን ህልውናን ማስቀጠል እንደሚቻል ብፁዕነታቸው አስገንዝበዋል፡፡
“በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ አስተምር በነበረበት ወቅት የንስሓ አባት ሆኜ አገለግላቸው የነበሩ ገንዘብ አሰባስበው በዛሬው ዕለት ለምርቃት የበቃውን የአብነት ትምህርት ቤት ሕንፃ በአጭር ጊዜ ውስጥ ገንብተው አስረክበዋል” ብለዋል፡፡
የተገነባው ሕንፃ ሙሉ በሙሉ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ችግር ባይፈታም እንደ ጅምር መልካም መሆኑን የገለጡት ብፁዕነታቸው ትልልቅ ካቴድራሎችን ከመሥራት አስቀድመን                በካቴድራሎች ሊያገለግሉ የሚችሉ ዘመኑን የዋጁ አገልጋዮችን አስተምረን ማውጣት የምንችልባቸውን የትምህርት ተቋማት ማጠናከር ይኖርብናል “ብለዋል፡፡
ከዚህ ቀደም የአብነት ተማሪዎች ቁራሽ ለምነው ይማሩ እንደነበር ብፁዕነታቸው አስታውሰው ተማሪዎቹ ትምህርታቸውን ብቻ እያሳቡ እንዲማሩ ለማድረግ በገቢ የሚደጉሙ ተዛማጅ የልማት ሥራዎች እየተሠሩ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የአብነት ትምህርት ቤቱን በዘላቂነት ለመደገፍ አራት የእህል ወፍጮ እና የወተት ሀብት ልማት ፕሮጅክት በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ ከፕሮጅክቶች ከሚገኘው ገቢ 40 በመቶው ለአብነት ትምህርት ቤቱ አገልግሎት የሚውል ይሆናል፡፡ በተለይ መንግሥት በሰጠው 6.6 ሄክታር መሬት በተቋቋመው የወተት ሀብት ልማት ፕሮጀክት የሚገኘው ገቢ ለተማሪዎቹ ልብስ ቀለብና የንጽሕና መጠበቂያ የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን ለሟሟላት እንደሚውል ብፁዕነታቸው ገልጸዋል፡፡
በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ተገኝተው ቡራኬ የሰጡት የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የደብረ ሮሐ ቅዱስ ላሊበላ ገዳም የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ “መኖር ለመሥራት፣ መሥራት፣ ደግሞ ለመኖር ሊሆን ይገባል፡፡ ለመኖር መሥራት ያስፈልጋል፡፡ በዚህ የአብነት ትምህርት ቤት ሕንፃ ግንባታ ላይ የተሳተፋችሁ በመሉ ለመኖር የሚያበቃችሁን ሥራ ሠርታችኋልና ደስ ይበላችሁ” ብለዋል፡፡
የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ሓላፊ ዶክተር ኂሩት ካሳው በበኩላቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያን የገነባችና እየገነባች ያለች መሆኗን ገልጠው ቀለም በጥብጣ፣ ብራና ዳምጣ፣ ብዕር ቀርጻ ትውልድ ስታስተምር መኖሯን አስረድተዋል፡፡
“ቤተ ክርስቲያን የራሷ ፊደል ባይኖራት ኖሮ ኢትዮጵያውያን ተለይተን የምንታወቅበት ማንነት ባልኖረን ነበር፡፡ ሀገር ሊገነባ የሚችለውም በዕውቀት፣ በጥበብና በትምህርት ብቻ ነው” ብሏል፡፡ ኢትዮጵያ ሀገራችን ስትመራባቸው የኖሩ ሕግጋት የተወሰዱት ከቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሀገርን እንደ ሀገር ለመምራት እንዲሁም ሕግ ለማውጣት መነሻ፣ የዕውቀትና የጥበብ መፍለቂያ መሆኗን ሓላፊዋ ገልጠዋል፡፡
“ለሀገራችን የዕውቀትና የጥበብ መነሻና የልህቀት ማእከል የሆኑት የአብነት ትምህርት ቤቶች በአደገኛ ሁኔታ ላይ እንዲገኙ ቸል ብለናቸዋል ያሉት ዶክተር ኂሩት የሀገራችንን ህልውናና ጥበብ የምናስቀጥልባቸውን የአብነት ትምህርት ቤቶች ልንደርስላቸው ይገባል በማለት አሳሳበዋል፡፡
የመቄት ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሃይማኖት ጋሹ “መቄት ወረዳ የታላላቅ ገዳማትና የበርካታ ጥንታዊ ቅርሶች መገኛ ናት፡፡ በአባታችን ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ ያስተማሯቸው ምእመናን ዘመናዊና ሁሉን አቀፍ የአብነት ትምህርት ቤት ሕንፃ ገንብተው ለመቄት ወረዳ ሕዝበ ክርስቲያን ማበርከት በመቻላቸው የተሰማኝ ደስታ የላቀ ነው፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቱ፣ የወተት ሀብት ልማት ፕሮጀክቱና የእህል ወፍጮ ልማቱ ዘላቂና አስተማማኝ እንዲሆን ወረዳው ክትትልና ድጋፍ ያደርጋል” ብለዋል፡፡
የአብነት ትምህርት ቤቱ ወደሚቀጥለው ትውልድ እንዲተላለፍ የምንችለውን ሁሉ እናደርጋለን፡፡ የአካባቢውም ሆነ የአብነት ትምህርት ቤቱ ተቀብሎት ለሚያስተምራቸው 70 ተማሪዎች መቀመጫ ወንበሮች እንዲሁም መብራትና ውሃ ለማስገባት በቅርቡ በወረዳ አስተዳዳሩ ስም ቃል እገባለሁ ብለዋል፡፡
የልማት ማኅበሩ ጸሐፊ አቶ ቻለው እንደሻው “የልማት ማኅበሩ በአባታችን በብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የተመሠረተ ሲሆን በመንፈሳዊ ትምህርት ቤቶች አገልግሎት ላይ እንድንሳትፍ አባታችን ባቀረቡልን ጥያቄ መሠረት በየወሩ ገንዘባችን በማውጣትና፣ ከበጎ አድራጊ ድርጅቶች ጋር በመነጋገር፣ ለቤተ ክርስቲያን አሳቢ አባቶችን በማነጋገርና ገቢ በማሰባሰብ ይህንን የመሰለ የአብነት ትምህርት ቤት ሕንፃ ለመገንባት ችለናል ብለዋል፡፡
ጥር ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦ በእግዚአብሔር ፈቃድ ግንባታው ተፈጽሞ በዛሬው ዕለት ለምርቃት በቅቷል፡፡ ማኅበሩ በቀጣይ የአብነት ትምህርት ቤት የሚያስፈልጋቸውን አካባቢዎች በመለየት ትምህርት ቤት ይሠራል፡፡ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን አጥቢያዎችና ገዳማት ይደግፋል ያሉት ጸሐፊው አጠቃላይ ፕሮጀክቱ ከ6.7 ሚሊዮን ብር በላይ መፍጀቱን ተናግረዋል፡፡
                              ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ቁጥር 14/ቅጽ25 ቁጥር 388 ከሰኔ16-30/ቀን2010ዓ.ም

 

ለአንዲት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሲኖዶስ

                              ለአንዲት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ሲኖዶስ!

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማኅበራት ኅብረት  በቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል ስለሚካሄደው እርቀ ሰላምና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ የተሰጠ መግለጫ፡፡

      ቅዱስ ሲኖዶስ ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ የሊቃነ ጳጳሳት፤ የጳጳሳት እና የኤጲስ ቆጶሳት አንድነት ጉባኤ  ነው፡፡ የዚህ መሠረቱ ደግሞ ጌታ በቅዱስ ወንጌል፣‹‹ከእናንተ ሁለቱ በምድር ላይ ስለሚለምኑት ነገር ሁሉ ቢተባበሩ በሰማያት ባለው አባቴ ዘንድ ይደረግላቸዋል ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰባሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና፤›› (ማቴ 18፡19) የሚለው አምላካዊ ቃል ነው፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ መሠረታዊ ዓላማውም፡

  • የቤተ ክርስቲያንን ዶግማና ቀኖና መጠበቅና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ማጽናት
  • ምእመናንን በመጠበቅ የእግዚአብሔር መንግሥት ወራሾች እንዲሆኑ ማብቃት (ዮሐ 21፥19)
  • ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የዲያብሎስን ውጊያ ተቋቁማ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት አገልግሎቷን እንድትፈጽም በፍቅር፣ በአንድነትና በትሕትና በመቆም የቤተ ክርስቲያንን አንድነት መጠበቅ ነው፡፡

ይሁንና ላለፉት ሁለት ዐሥርት ዓመታት በስንዴው መካከል እንክርዳድ የሚዘራው ጠላት ዲያቢሎስ የኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር አንድነትን በማፋለስ በአበው ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ልዩነት በመፍጠር የዶግማና ቀኖና ልዩነት ሳይኖር ሲኖዶሱን እስከ መክፈል የደረሰ አሳዛኝ ተግባር መፈጸሙ መላውን ማኅበረ ምእመናን ሲያሳዝን የኖረ ተግባር ከመሆኑም በላይ በቀደመ ታሪኳ ታላቅ በሆነችው ቤተ ክርስቲያናችን ላይ ጥቁር ነጥብ የጣለ ድርጊት ሆኖ በትውልድ የሚታወስ ነው፡፡

ይህ ተግባር የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በሚፈለገው ደረጃ እንዳይካሄድ፣ ቅሬታዎች እንዲነሡ፣ ምእመናን እርስ በርስ እንዳይተማመኑና አንድነታቸው እንዳይቀጥል አድርጎአል፡፡በተጨማሪም  የቤተ ክርስቲያኒቱ የዕውቀት ምንጭ የሆኑት የአብነት መምህራን እና ተማሪዎች መሰደድ፤ ምእመናን ወደ መናፍቃን ጎራ መቀላቀል፤ሕገ ወጥነት እና ግለሰባዊነት እንዲስፋፋና የቡድን አመራርና ጣልቃ ገብነት እንዲሰፍን አድርጓል፡፡ይባስ ብሎም በአስመሳይ አገልጋዮች የተሐድሶ ኑፋቄ መሰራጨትን አስከትሏል፡፡

በመሆኑም እኛ በቊጥር ከ100 (ከመቶ)በላይ የሆኑ ማኅበራትን የያዝን የኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን የመንፈሳዊ ማኅበራት ኅብረት ሥራ አስፈጻሚዎች በቤተ ክርስቲያን በተለያየ መዋቅር ውስጥ እውቅና ተሰጥቶን የምናገለግልና በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ በተለያየ ሙያ የተሠማሩ አባላትን የያዝን ሲሆን በቤተ ክርስቲያን እርቀ ሰላምና በተያያዥ ወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ የሚከተለውን የአቋም መግለጫ አውጥተናል፡፡

1.በአንዲት፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊት እና ዓለም አቀፋዊት ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ባሉ አባቶቻችን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል የነበረው የልዩነት ግድግዳ ፈርሶ፣ይቅርታን የሚያስተምሩን አባቶቻችን ራሳቸው ይቅር ተባብለው መልካም አርዓያነታቸውን ለእኛ ለልጆቻቸው እንዲያሳዩን እንፈልጋለን፡፡ሰላምንና ይቅር መባባልን የሚሰብኩን አባቶቻችን እንዲሁም ደግሞ ራሳቸው በተግባር ኑረውት እንዲያሳዩን እኛ የመንፈስ ልጆቻቸው አጥብቀን እንሻለን፡፡ በአባቶቻችን እርቀ ሰላም ቀደም ሲል በተፈጠረው መለያየት ግራ የተጋቡትና የተበታተኑ ምእመናንን በፍቅር ለመሰብሰብ እንዲችሉ ትልቅ ተስፋ እንዳለው እናምናለን፡፡

2.በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ አባቶች ይህንን የእርቀ ሰላም ጥሪ ተቀብለው ተግባራዊ እንቅስቃሴ በመጀመራቸው ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡ይህንን የተቀደሰ ዓላማ ይዘው የተነሡ የእርቀ ሰላም ኮሚቴ አባላትን እናደንቃለን፡፡ እኛም በቤተ ክርስቲያን በተለያየ መዋቅር አገልግሎት የምንሰጥ ማኅበራት አባላት በግልም እንደ ማኅበርም እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን የተጀመረው የእርቀ ሰላም እንቅስቃሴ ከግብ እንዲደርስ በማንኛውም አገልግሎት ለመደገፍና ለእርቀ ሰላሙ ከሚጥሩ አካላት ጎን ለመቆም ዝግጁ መሆናችንን እንገልጻለን፡፡

3. ይህንን የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት ለመመለስ እና የሀገራችንን ሕዝቦች በሰላም መኖር ለማረጋገጥ የሚደረጉ ማንኛቸውንም ጥረቶች ሁሉ እንደግፋለን፤መንግሥት ይልቁንም የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ በዚህ ረገድ እያሳዩ ያለውንም ፍላጎት እናደንቃለን፡፡

4. በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል በተፈጠረ አለመግባባት ለ፳ዓመታት ያህል ተለያይቶ የቆየውን የሁለቱ ሀገር ሕዝቦች አንድ ለማድረግ እየተደረገ ያለውን ጉልህ እንቅስቃሴና ሐምሌ 1ቀን 2010 ዓ.ም በአሥመራ ከተማ ላይ ኤርትራዊያን ወገኖቻችን የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድን በደማቅ ሁኔታ በመቀበል ለኢትዮጵያዊያን ያላቸውን ፍቅር የገለጹበት መንገድ እጅግ ልብ የሚነካ በመሆኑ በታላቅ ትሕትና ያለንን አክብሮት እንገልጻለን፡፡መንግሥት ከሚያደርገው ጥረት ጎን ለጎን በሁለቱም ሀገር ያሉ አባቶቻችን ሊቃነ ጳጳሳትም በሁለቱ ሀገር ሕዝቦች መካከል የተጀመረው ግንኙነት እና በሁለቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያለው ግንኙነት ተጠናክሮ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በጋራ በምናካሄድበት ሁኔታ ላይ ጉልህ ድርሻ እንዲኖራቸው ጥሪያችንን እናስተላልፋን፡፡

5.የኢትዮጵያ መንግሥትና የኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በሊቢያ ሰማዕትነት የተቀበሉ ኢትዮጵያዊያን እንደ ግብፅ ሰማዕታት ተገቢውን ትኩረት አግኝተው አጽማቸው በሀገራቸው በክብር የሚያርፍበትና እንደ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ተገቢው መታሰቢያ የሚደረግበት ሁኔታ እንዲኖር አበክረን ጥሪ እያስተላለፍን በዚህ ረገድ የማኅበራት ኅብረታችን የድርሻውን ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ለመግለጽ ይወዳል፡፡

6. የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን አቋምና አስተምህሮ በማይመጥን መልኩ የሚካሄዱትን አድሏዊ አሠራሮች፣ የሙስናና ብልሹ አሠራርን ለማስወገድ ቋሚ ሲኖዶስና ቅዱስ አባታችን የጀመሩትን በተለይም በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ውስጥ የተደረገውን ጅምር አስተዳደራዊ ለውጥ እንዲሁም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ የተናገሩትን ተስፋ ሰጪ ቃላት እንደግፋለን፡፡ በቀጣይም  ከችግሮች ውስብስብነት አንጻር በአስተዳደር በኩል ያለውን ክፍተት አባቶቻችን በቅዱስ ሲኖዶስ መክረውበት የማያዳግም ሥር ነቀል ለውጥ እንደሚያመጡ የምናምን ሲሆን እኛ የኅብረቱ አባላት በሙያም ይሁን በሌላ አስፈላጊ በሆነ መልኩ ድጋፍ ለመስጠት ዝግጁ መሆናችንን እንገልጻለን፡፡

7. በአጠቃላይ በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንም ይህ የተጀመረው የዕርቀ ሰላም ጥረት በምንም ምክንያት ወደኋላ እንዳይመለስ በጸሎትም በሐሳብም የበኩላቸውን አስተዋፅዖ እንዲያደርጉ ጥሪ እናስተላልፋለን፡፡

8.በዚሁ አጋጣሚ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም የተቋቋሙ የተለያዩ የአገልግሎት ማኅበራት ሁሉ የጋራ መናበብ እና እቅድ ኖሯቸው ተጨባጭ ለውጥ በሚያመጡበት ስልት ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያናችን እድገት በጋራ እንዲያገለግሉ ጥሪአችንን እናስተላልፋለን፡፡

                                                                ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

                                     በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን የመንፈሳዊ አገልግሎት ማኅበራት ኅብረት

                                                                ሐምሌ 2 ቀን 2010 ዓ.ም፣ አዲስ አበባ  

 ኀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ- የአንተ በሆነ መንፈስ ቅዱስ አንድ መሆንን ስጠን!

በዐለም የክርስትና ታሪክ ውስጥ ምእመናን  ከተፈተኑበት ፈተናዎች አንዱ በአንድ በታወቀ መንበር ላይ ከአንድ በላይ ፓትርያርኮች ወይም ፖፖች መሾም ነው፡፡በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ቀድሞ በነበረ ፓትርያርክ ወይም ፖፕ ለመጀመሪያ ጊዜ ተደርቦ እንደተሾመ የሚነገርለት ቅዱስ አቡሊዲስ ዘሮም ነው፡፡ ቅዱስ አቡሊዲስ (Hippolytus) ተቀናቃኝ ፖፕ የሆነበት መንገድ ከዘመኑ የተነሣ በታሪክ ብዙም ባይገለጽም ተቀናቃኝ ሆኖ የተሾመው ግን ካሊክሰቶስ ቀዳማዊ (Pope Callixtus I) የሮም ፖፕ በነበረበት ዘመን ነበር፡፡ ሆኖም ካሊክስቶስ ሲያልፍ በወንበሩ ከተተካው ከፖፕ ፖንትያን (Pope Pontian) ጋር ታርቆ ችግራቸውን ፈትተዋል፡፡ በመጨረሻም ያረፈው በሰማዕትነት ስለነበረ ተጋድሎው በቅድስና ይታሰባል፡፡ በሮም ካቶሊክ ዘንድ በዓሉ የሚከበርለት ከታረቀው ከፖፕ ፖንትያን ጋር በአንድነት በእነርሱ አቆጣጠር ኦገስት በሚባለው ወራቸው በ13ኛው ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ዕርቅን አውርዶ ችግርንም ፈትቶ በአንድነት መከበርና መታሰብ የጀመረው ከመጀመሪያው ዐለምአቀፍ ጉባኤ ከጉባኤ ኒቅያ አንድ መቶ ዐመት በፊት ገና ሦስተኛው ክፍለ ዘመን  መጀመሪያ ላይ እንደነበረ ታሪካዊ አስረጅ አለው ማለት ነው፡፡

በርግጥ በፖፕ ላይ ፖፕ እየተሾመ መወዛገብ በሮማ ካቶሊክ ታሪክ ደጋግሞ ያጋጠመ ነገር ነበር፡፡አጥኝዎች እንደሚሉት በሮም ካቶሊክ ታሪክ ይህ ችግር ለ42 ጊዜ ያህል ተከስቷል፡፡ ሆኖም ከፍተኛ ውዝግብ ያስከተለው በ14ኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ የተከሰተውና ለ40 ዐመታት የቆየው ታላቅ ውዝግብ ነው፡፡ከ1378 -1417 እንደቆየ የሚነገርለት ይህ ክፍፍል በሮማ ካቶሊክ ታሪክ ትልቁና በታሪክ ተመራማሪዎችም ዘንድ ትልቁ የምዕራቡ ክፍፍል እየተባለ የሚጠራና ከሦስት በላይ ፖፖች እኔ ነኝ ሕጋዊ ፖፕ በማለት የተወዘጋቡበት ነበር፡፡ መነሻውም በግልጽ ፖለቲካዊ ጣልቃገብነት የፈጠረው እንደነበር ይታወቃል፡፡ቢሆንም ከ1414 – 1418 ኮንስታንስ ላይ በተካሔደ ጉባኤ ችግሩን ፈትተው አንድነታቸውን ለመመለስ ችለዋል፡፡

በምሥራቁም ዐለም ድርጊቱ በተለያዩ ጊዜያት ሲከሰት ኖሯል፡፡ለምሳሌ በቁስጥንጥንያው ንጉሥ ታግዞ በእስክንድርያ መንበር  በቅዱስ አትናቴዎስ ላይ ተተክቶ የነበረው ጊዮርጊስ በእኛ ሊቃውንት ዘንድም በደንብ የሚታወቅ ታሪክ ነው፡፡ ቆይቶ ደግሞ በተለይ ከጉባኤ ኬልቄዶን በኋላ በአንጾኪያ እና በቁስጥንጥንያ መንበሮች ብዙ ውጣ ውረዶች መፈራረቆችና መተካካቶች መሳደዶች በተደጋጋሚ አጋጥመዋል፡፡

በቅርብ ጊዜ እንኳ በሩስያ፣በሕንድ እና በአርመን ኦርቶዶክሶች ተከስተው የነበሩት መከፋፈሎች ሊዘነጉ የሚችሉ አይደሉም፡፡ብዙዎቹ ወይም ሁሉም ልዩነቶች ተፈትተዋል፡፡ በግሪክ ኦርቶዶክስ ግን አሁንም ትልቅ ክፍፍል አለ፡፡ ሆኖም የእነርሱ ፖለቲካዊ ጫና የፈጠረው ሳይሆን የትውፊት መለወጥ ነው፡፡ ይኸውም የቀድሞውን ዮልዮሳዊ የዘመን አቆጣጠር ትተው በምዕራባዊ ጎርጎርዮሳዊ አቆጣጠር መጠቀም ሲጀምሩ ይህንን የተቃወሙት ለብቻቸው ተለይተው ወጥተዋል፤ ስማቸውም ኦልድ ካላንደሪስት ኦርቶዶከስ ቤተ ክርስቲያን (Old Calendarists orthodox Church) የሚል ነው፡፡

እነዚህ ሁሉ የሚያመለክቱት በፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ምክንያት በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ላይ መለያየትና መከፋፈል በሌሎቹም ላይ ቀደም ብሎ ያጋጠመ እና ሲፈቱት የኖረ ችግር መሆኑን ነው፡፡ ሆኖም በሮም ለ40 ዐመታት የቆየው ውዝግብ ግን ብዙ ችግር ያስከተለ ከመሆኑም በላይ የተፈታበትም መንገድ ብዙ ትምህርት ሊወሰድበት የሚችል ነገር ነው፡፡ ምክንያቱም ወቅቱ ገና ከሉተር መነሣት በፊት ስለነበረ መላው ምዕራብ አውሮፓ በሮም ካቶሊክ ውስጥ ነበር፡፡ የመጀመሪያዎቹ ተወዛጋቢ ፖፖች ደግሞ ትውልዳቸው አንዱ ከፈረንሳይ ሌላኛው ከጣልያን ነበሩ፡፡ ይህም ማለት ተፎከካሪዎቹ ፖፖች በሁለት ሀገርና መንግሥታትም ጭምር ስለሚታገዙ ክፍፍሉ ጠንካራ ነበር፡፡ መንግሥቶቻቸው ደግሞ ሌሎቹን ሀገሮች እየቀሰቀሱ ከፊል የምዕራብ አውሮፓ መንግሥታት አንዱን ሌሎቹ ደግሞ ሌላውን ይደግፉ ስለነበር የጣልቃገብነቱንና ፍላጎት ያለው አካል ብዛትን ስናይ ብዙ ችግሮች እንደነበሩበት ለመረዳት አያዳግትም፡፡ ለአንዳንዶች ሌሎች ሦስተኛና አራተኛ ፖፖችን እስከመሾም ያደረሳቸውም ከዚህ ከመጀመሪያዎቹ የኃያላን መንግሥታት ፍላጎት የተላቀቀ አዲስ ሲሾም ይፈታል ብለው በማሰብ ነበር፡፡ ሆኖም አልተሳካም፡፡ በመጨረሻ ግን አራት ዐመት በወሰደው ጉባኤያቸው ሁሉንም መንግሥታት፤ ካርዲናሎች፤ ሕዝቡን፤ ደጋፊዎቻቸውንና የመከፋፈል ተጠቃሚዎች የነበሩትን ሁሉ አሳምነውና  አሸንፈው አንድ መሆን  በቁ፡፡ በእውነት ከሆነ እንኳን በቁጥር ከዐሥር በላይ የሆነ ሀገርና መንግሥታትንና ሕዝብ አሸንፈው ለዚህ ከመብቃት በላይ አስደናቂ ነገር የለም፡፡

በእኛ ሀገር የተከሰተውም ምክንያቱ ፖለቲካን ተገን ያደረገ እንደነበር ግልጽ ነው፡፡ ሆኖም ፖለቲካን ተገን አድርጎ ቤተ ክርስቲያንን መጉዳት ሲጀመር ይህ የመጀመሪያው አልነበረም፡፡ ከደርግ መምጣት ጋር ተያይዞ ባለ ትልቅ ራእይ በነበሩት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ የተፈጸመው ግፍ ቢያንስ መንበሩ ወደ እኛ ከመጣ በኋላ ላለው ታሪካችን የመጀመሪያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ምንም እንኳ በየዋሕነት ለነበሩትና በእንዲህ ያለ ጊዜ ምን መደረግ እንዳለበት ግንዛቤ እንዳልነበራቸው ግምት በምንወስድላቸው አባቶች ላይ ሙሉ በሙሉ ለመፍረድ ቢያስቸግርም ፖለቲካዊ ሒደቱን ተቋቁሞ በሐዋርያዊ መንገድ ችግሩን ለመወጣት የተደረገ ጥረት ግን ጎልቶ አይሰማም፡፡ እንዲያውም የፖለቲከኞችን ተንኮል ካለመገንዘብም ይሁን ከሰብአዊ ድካም በመነጨ በማይታወቅበት መንገድ ባይብራራም ተወቃሽ ተደርገው ሲቀርቡም ይስተዋላል፡፡

የደርግ ዘመን አብቅቶ ኢሕአዴግ ሲገባም ግቡ ተመሳሳይ የሆነ ነገር ግን በመንበሩ ላይ በነበሩት አባት የወደፊት ሁኔታ ላይ ግን ለየት ያለ ድርጊት ተፈጸመ፡፡ በቀደመው ዘመን በአቡነ ቴዎፍሎስ የነበረውም ድርጊት ተወገዘ፡፡ ሆኖም የቀደመውን ድርጊት አውጋዦቹ ሌላ ተመሳሳይ ድርጊት ላለመፈጸማቸው ዋስትና ከመሆን ይልቅ የሚያወግዙትን ድርጊት አሻሽለው ከመፈጸም አልተመለሱም፡፡ በዚህ ወቅት የነበሩት አባቶችም አሁንም ከሐሜት መትረፍ አልቻሉም፡፡ ሐሜታውም በሀገር ውስጥም በውጭም ያሉትን የሚያጠቃልል ነው፡፡

ታሪኩን በዚህ መጠን ለማስታወስ ያህል የሞከርነውም የችግሩ ተጠያቂነት በሁሉም ላይ ያረፈ መሆኑን ለመጠቆም ያህል እንጂ በታሪኩ ላይ ለመነታረክ አይደለም፡፡ ይልቁንም በተጠያቂነት ከመጠየቅ አልፈን ታሪካችንን ለሚያድስና ያለፈውን ለትምህርት ብቻ እንድንተወው የሚያደርግ አዲስ ወርቃማ ዕድል በእጃችን መኖሩን አስተውለን ሁላችንም በኅብረተ መንፈስ ቅዱስ አንድ እንድንሆን የምንጸልለውን ጸሎት በተግባር እንድናውለው ለመጠየቅ ያህል ብቻ ነው፡፡

በዚህ መልእክታችንም በቅዳሴያችንና በዘወትር ጸሎታችን የምንጸልያቸውን መነሻ አድርገን ልናደርጋቸው የሚገቡንን በማስታወስ መልእክታችንን ለማቅረብ እንወዳለን፡፡

                 ሀበነ እግዚኦ አእይንተ አእምሮ

አባቶቻቸን አርእስተ መናብርቱ፣ በሁሉም በኩል ያሉ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ጳጳሳትና ካህናት በሙሉ ቅዳሴ እግዚእን በሚቀድሱበት ጊዜ ሓዳፌ ነፍስ ወይም ነፍስን የሚያጸዳ የሚወለውል ተብሎ በሚጠራው የመጨረሻው ጸሎት ላይ “ኀበነ እግዚኦ አእይንተ አእምሮ ወትረ ኪያከ ይርአያ ወአእዛንነሂ ቃለ ዘባሕቲትከ ይስምዐ” ‘አቤቱ ጆሮዎቻችን የአንተን ቃል ብቻ ይሰሙ ዘንድ ዐይኖቻችንም አንተን ብቻ ያዩ ዘንድ የዕውቀትን የማስተዋልን ዐይኖች ስጠን’ እያሉ ስለራሳቸውም ስለ እኛም ይጸልያሉ፡፡እኛም ልጆቻችሁ ዛሬ ሌላ መልእክት የለንም፡፡ እንደምትጸልዩልን እንደምትለምኑልን ልክ እንደዚያው የሌሎችን ቃል ትታችሁ የጌታችንን ቃል ሰምታችሁ አስታውሳችሁ አንድ ሁኑልን ብቻ ነው የምንለው፡፡የእርሱን ቃል ደግሞ ልትዘነጉት አትችሉም፡፡የጌታችን ቃሉ ደግሞ ትናንት በተፈጠረው በታሪኩ ላይ እንድንነታረክና እንድንከራከር አይፈቅድልንም፡፡ ይልቁንም “ወንድምህን እስከ ሰባ ጊዜ ሰባት ይቅር በለው” እያለ የትላንቱን እንድንተወው ግዴታ ይጥልብናል እንጂ፡፡ እራሱም ጌታችን አስቀድሞ ሰይጣን ይህን ሊያደርገው ደጋግሞ የሚሞክረው መሆኑን “ስምዖን ስምዖን ሆይ፥ እነሆ፥ ሰይጣን እንደ ስንዴ ሊያበጥራችሁ ለመነ፤ እኔ ግን እምነትህ እንዳይጠፋ ስለ አንተ አማለድሁ፤ አንተም በተመለስህ ጊዜ ወንድሞችህን አጽና” (ሉቃ 22 ፥31-32)ሲል እንደገለጸልን ይህ የመለያየት ነገር የሰይጣን ነው፡፡ በመከራ ጊዜ ደግሞ እንደተጻፈው ብዙ ሰው ይፈተናል፡፡ በወቅቱ የድርጊቱ ተሳታፊዎች ባለመሆናችን የምንተቸው ሰዎች ሁሉ በቦታውና በጊዜው ብንኖር ኖሮ ከዚህ የከፋ ልናደርግ እንደምንችል ገምቶ ራስንም በእነርሱ አስገብቶ ይቅር ማለት ተገቢ ነው፡፡ ከዚህ አልፎ  እነ እገሌ ናቸው ተጠያቂ በሚል መንገድ መተቸት ነገሩን ከማባባስ ያለፈ የሚፈጥረው ፋይዳ የለም፡፡ በርግጥም እንዲህ ያለው ልዩነት ምእመናን በክርስትናቸው የሚበጠሩበት ነው፡፡ ጌታችን ግን በአንጻረ ቅዱስ ጴጥሮስ “እምነትህ እንዳይጠፋ አማለድሁ” ብሎ በሥጋዌው ቤዛ ሆኖ ያቀረበልንን የጸሎት መሥዋዕት ምልጃ ብሎ በመጥራት ነግሮናል፡፡ ይኸውም “ቅዱስ አባት ሆይ፥ እነዚህን የሰጠኸኝን እንደ እኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው”(ዮሐ17፥11) የሚለው ነው። ስለዚህ በቅዳሴያችን  ላይ ጆሮቻችን የአንተን ቃል ብቻ ይሰሙ ዘንድ ካላችሁ አይቀር ቃሉ አንድ ይሁኑ የሚል ስለሆነ አንድ ትሆኑልን ዘንድ በታላቅ ትሕትና እንጠይቃለን፡፡

በርግጥም ልንሰማውና ልንከተለው የሚገባን የእርሱ ቃል ብቻ መሆን አለበት፡፡ በቤተ መቅደስ በቅዳሴ ጊዜ “ባርክ ላዕለ አባግዐ መርኤትከ፤ ወአብዝኀ ለዛቲ አጸደ ወይን እንተ ተከልካ በየማንከ ቅዱስ” እያላችሁ ምእመናንን ለማብዛትና ለመጠበቅ ፈቃዳችሁ ጸሎታችሁ መሆናችሁን ሁልጊዜ ትገልጻላችሁ፡፡”ባርኮ ለዘንቱ ኅብስት … ወሚጦ ለዝንቱ ጽዋዕ … ” እያላችሁ ቅዱስ ምስጢርን እንዲፈጸምላችሁ ትማጸኑታላችሁ፡፡ ያለ እርሱ ሊሆን ሊፈጸም የሚችል አይደለምና፡፡ ታዲያ ለምሥጢራት የምንጠራውን ጌታ ምሥጢራቱን ለሚፈጽሙት አበው አለመግባባት እንዴት ልንዘነጋው እንችላለን? በዚያ ጊዜ ብቻ ይህን አድርግ ብለን ለምነነው ይህን ጉዳይ ግን ብቻችንን ወይም ደግሞ ፖለቲከኞችንና ሌሎች የልዩነት ተጠቃሚዎችን ይዘን እንፈታዋለን ልንልምአንችልም፡፡እንግዲያው ጆሮዎቻችን እንደምንጸልየው የእርሱን ቃል ብቻ የሚሰሙበት፤ዐይኖቻችንም እንደ ምልጃ ጸሎታችን እርሱንም ብቻ ሊያዩበት እና ሌሎች ጊዜያዊ ነገሮችንና ፐሮፓጋንዳዎችን ቸል ሊሉበት የሚገባው እውነተኛው ጊዜ ዛሬ መሆን አለበት፡፡ ለወጡት ሚጠት (መመለስ)፣ለባዘኑት ዕረፍት፣ ለሚጨነቁት መረጋጋት፣ በግጭትና በዕልህም ውስጥ ላሉት ሰላምና አንድነት፣ ለቤተ ክርስቲያን አንድነት እና ለምእመናን ኅብረት ይሆን ዘንድ በእውነት ሌሎችንን ተጽእኖዎች ሁሉ ተቋቁመን መገኘት ይገባናል፡፡ ከዚህ ውጭ ከሆንን ግን”በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ”(ሐዋ፳ ፥፳፰) በሚለው ቃለ ሐዋርያ መወቀሳችን የማይቀር ይሆናል።

                 አድኅን እግዚኦ ዛተኒ ሀገረ

  የአባቶች አንድነት ለሀገር አንድነትና ሰላም ያለውም አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑ የማይጠረጠር ነው፡፡የጥላቻ፣ የወቀሳና የከሰሳ ፖለቲካ ወደ ኢትዮጵያውያን ልብ ዘልቆ ከገባበት ከላፉት ስድሳ ዓመታት ወዲህ ጥላቻና መለያየት፤መሰዳደብና መወጋገዝ፣ በቀልና ግድያ፣ ተንኮልና ሴራ ሲጨምር እንጂ ሲቀንስ አልታየም፡፡ ብሔራዊ መግባባት በተወሰነ ደረጃ በሚቀነቀንበት በአሁኑ ሰዓት እንኳ በሰላም አልባሳት የተደበቁ የበቀል ድምፆች ከአንዳንዶች የሚሰሙ መሆኑን ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ ታዲያ እንደዚህ ባለጊዜ ዐለምን በሙሉ ወደ ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ ለማቅረብ አደራውን ለተቀበሉ አባቶች ሓላፊነቱ ግልጽ ነው፡፡ ” … ሰላማዊ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላመከ ኀበነ ወአጽንዕ ለነ ሰላመከ” ብለን በየቅዳሴያችን እየለመንነው ሰላም አጣን ብንል ሁሉም ይታዘበናል፡፡ ምክንያቱም እኛ ካልገፋናት በስተቀር የእርሱን ሰላም ከእኛ ማንም ሊወስዳት አይችልምና፡፡

ይልቁንም እኛ ፍጹም ሰላም ሆነን ሀገራችንም ከየትኛውም ችግር እንድትወጣ በእውነት መጣር ይኖርብናል፡፡ በዐርብ የሊጦን ጸሎታችን “አድኅን እግዚኦ ዛተኒ ሀገረ ወካልኣተኒ አኅጉረ ወበሐውርተ እለ በሃይማኖተ ዚአከ የኀድሩ” ‘አቤቱ ይህች ሀገር እና አንተን በማመን የሚኖሩ ያሉባቸውን በዐለም ላይ ያሉ ሌሎችን ሀገሮችም ሁሉ አድን’ እያልን የምንማልድ ሰዎች በእኛ ልዩነት ምክንያት ሕዝበ ክርስቲያኑን ለያይተን፣በብዙ ውስብስብ ችግሮች ውስጥ አስገብተን ፣ በአንድ ቤት ሳይቀር ባልና ሚስት፤ ታላቅና ታናሽ ተለያይተው ጸሎቱ ምልጃው እንዴት ስሙር ሊሆን ይችላል፡፡ ሌላው ቀርቶ በልዩነቱ ምክንያት ሰብሳቢ አጥተው ባዝነው ከመንጋው እየተለዩ ወደሌሎቹ በረቶች ምንያህል ነፍሳት እንደሔዱ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ እንኳን    ከምእመናን መምህራንና አገልጋይ ከሚባሉት አንኳ ምን ያህሉ በነፍስ ተጨነቁ፤ ስንቶቹስ ባዘኑ፡፡ ስለዚህም ጸሎታችንን በተግባር እንግለጠው፡፡ያ ካልሆነ አቤቱ ሀገራችን አድን ስንለው ልዩነቱንና መለያየቱን እናንተ በተግባር አገዛችሁት እንጂ መች ተጸየፋችሁት የሚያስበለን ይመስላል፡፡ ስለዚህም ስለሀገራችንም፣ ስለሕዝበ ክርስቲያንም አንድነት ስንል አንድነቱን ያለ ቅድመ ሁኔታ በይቅርታ እና በዕርቅ ልንዘጋው ይገባናል፡፡ በዘመናችን የሀገራችን ፖለቲካዊ ችግሮች ለመፍታት ፖለቲከኞች ለሚሔዱበት የዕርቅና የሰላም ጉዞ አርአያ መሆን እንኳ ባይቻለን ፍኖተ ሣህሉን ለመከተል እንኳ ካልቻልን ጌታችን አይሁድን በዚህ ትውልድ ንግሥተ አዜብ ትፈርድበታለች እንዳለ በእኛም ላይ በመጨረሻው ዘመን የሚያስፈርድብን በእኛው ፖለቲከኞች መሆኑ የማይጠረጠር ነው፡፡ እነርሱ ከእኛ በብዙ መንገድ ተሽለው ተገኝተዋልና፡፡

          በኵሉ ልብ ናስተብቊዖ ለእግዚአብሔር አምላክነ

ይህ ይሆን ይፈጸም ዘንድ ጸሎት እንደሚደርግ የታመነ ነው፡፡ይልቁንም አሁን ደግሞ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት”አመንኩ በዘነበብኩ”‘በተናገርሁት(በጸለይኩት) አመንኩ’ የአመንኩትንም ጸለይኩ፤ መሰከርኩ (መዝ115፥1)እንዳለው የምንጸልየውን የበለጠ አስተውሎ መፈጸም ሳይጠይቅ አይቀርም፡፡ይህን የምናስታውሰው አይደረግም ለማለት ሳይሆን አሁንም በምንቀድሰው ቅዳሴ ዲያቆኑ አስቀድሞ “ያማረ በመንፈስ ቅዱስ የሚፈጸም አንድነትን ይሰጠን ዘንድ እግዚአብሔር አምላካችን በፍጹም ልብ እንለምነው” ሲል የታወቀውን በአዋጅ እንደሚያነቃን እንደሚያስታውሰው ያለ የልጅነት ማስታወሻ ብቻ ነው፡፡ እናንተም “ኀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ” ‘የአንተ በሆነ መንፈስ ቅዱስ አንድ መሆንን ስጠን’ የምትሉትን በተግባር ማየት የማይመኝ የለም፡፡ይልቁንም በዐርብ ሊጦን ጸሎታችን “ሀበነ ከመ በአሐዱ ልብ ወበአሐዱ አፍ ንሰብሕ ለአብ ወወልድ መንፈስ ቅዱስ ይእዜኒ ወዘልፈኒ ወለዓለመ ዓለም” ስትሉ እንደምትማልዱት በአንድ ልብ እና በአንድ አፍ በአንድ መቅደስና በአንድ ቅዳሴ አንድ ላይ ሆናችሁ ለፈጣሪ ምስጋና ስታቀርቡ ለማየት አብዝተን የምንመኝና የምንጸልይ እርሱንም “በፍጹም ልብ”ይሁን የምንል መሆናችንን ለሁላችሁም በታላቅ ትሕትና እናቀርባለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 ምንጭ፤ሐመር    መጽሔት    26ኛ ዓመት ቊጥር 2፤ሰኔ2010 ዓ.ም