የሆሣዕና ምንባብ13(ዮሐ.12÷12-20)

በማግሥቱም ለበዓል መጥተው የነበሩ ብዙ ሰዎች ጌታትን ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚመጣ በሰሙ ጊዜ÷ የዘንባባ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው “ሆሣዕና በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ÷ የእስራኤልም ንጉሥ ቡሩክ ነው” እያሉ ወጥተው ተቀበሉት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም የአህያ ውርንጫ አግኝቶ በእርስዋ ላይ ተቀመጠ፡፡ “የጽዮን ልጅ ሆይ÷ አትፍሪ፤ እነሆ÷ ንጉሥሽ በአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ይመጣል” ተብሎ እንደ ተጻፈ፤ ደቀ መዛሙርቱም አስቀድመው ይህን ነገር አላወቁም፤ ነገር ግን ጌታችን ኢየሱስ ከከበረ በኋላ በዚያ ጊዜ ይህ ነገር ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ÷ ይህንም እንደ አደረጉለት ትዝ አላቸው፡፡ ከዚያም አብረውት የነበሩት ሕዝብ አልዓዛርን ከመቃብር እንደ ጠራው÷ ከሙታንም እንደ አስነሣው መሰከሩለት፡፡ ስለዚህም ነገር ሕዝቡ ሁሉ ሊቀበሉት ወጡ፤ ይህን ተአምራት እንደ አደረገ ሰምተዋልና፡፡ ፈሪሳውያንም እርስ በርሳቸው÷ “የምታገኙት ምንም ጥቅም እንደሌለ ታያላችሁን? እነሆ÷ ዓለም ሁሉ ተከትሎታል” ተባባሉ፡፡