ተዝካረ ልደቱ ለኤልያስ ነቢይ

ኀዳር ፴፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ቅዱሳት መጻሕፍት ነቢዩ ኤልያስ የተወለደው በታኅሣሥ ፩ ቀን ከነገደ ሌዊ እንደሆነ ይገልጻሉ፤ የአባቱ ስም ኢያስንዩ የእናቱ ስም ቶና ይባላሉ፡፡ በተቀደሰች የልደት ቀኑም አባቱ ብርሃን የለበሱ አራት ሰዎች ሲሰግዱለትና ሕፃናት በሚጠቀልሉበት ጨርቅ ፈንታ በእሳት ሲጠቅልሉት  ተመልክቷል፡፡ (መጽሐፈ ስንክሳር ዘኅዳር ፩፣ መዝገበ ታሪክ ገጽ ፹፬)

ኢትዮጵያ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በተአምኆ ቅዱሳን መጽሐፉ ስለዚሁ ነቢይ እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ “ቴስቢያዊ (የቴስቢያ ሰው)፤ ኮሬባዊ (ወደ ኮሬብ ተራራ የወጣ)፣ ታቦራዊ (በታቦር ተራራ የተገኘ)፣ ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን የለጐመ ለሆነ፣ የጸሎቱ ቃልም በአዶናይ ዦሮ ውስጥ ለተሰማ፣ ውኃውን እስኪበላ ደርሶ እሳትን ከሰማይ ያወረደ ለሆነ፣ በእሳት ሠረገላ ተጭኖ ወደ ተድላ ደስታ ቦታ ለገባ ለነቢዩ ለኤልያስ ሰላምታ ይገባል።”

ሊቁ አርከ ሥሉስም በአርኬ መጽሐፉ ላይ ደግሞ እንዲህ ብሏል፤ “ምድራዊ የሆነ የዓለም ሕይወትን አራግፈህ ለማረፍ ወደ ሰማያት ያረግህ ለሆንክ ለአንተ ለኤልያስ ሰላም እላለሁ፡፡ አክአብን ለተናቀ ሥራው እየዘለፍከው ጣዖታትን የቀጠቀጥክ ማምለኪያዎቹን ያፈረስክ በምስጋናህ ምንኛ ተመሰገንህ።”

ቅዱሱ መጽሐፍ የዚህን ፈፍ  ነቢይ ስም “ኤልያስ” ፻ (መቶ) ጊዜ ጠቅሶታል፡፡ ድንቃ ድንቅ ተአምራቱንም መዝቦት እናገኛለን፤ ከእነዚህም መካከል አክአብና ኤልዛቤል ጣዖት በማምለከታቸው ኤልያስ ሦስት ዓመት ከ ስድስት ወር ዝናብን በጸሎቱ አቁሟል፡፡ (፩ኛ ነገ. ፲፯)፤ የሰራጵታዋን መበለት የሞተ ልጇን አስነሥቷል፡፡ (፩ኛ ነገ.፲፯፥፲፱)

ለአምላካችን እግዚአብሔር ያቀረበውን መሥዋዕት እሳት ከሰማይ ወርዶ የበላለት ነቢይ እንደሆነም መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፤ (፩ኛ ነገ ፲፰) ከሦስት ዓመት ከስድስት ወር በኋላ ቀርሜሎስ ወጥቶ በመጸለይ ዝናብ እንዲዘንብ አድርጓል፤ (፩ኛ ነገ. ፲፰) አካዝያስ የላካቸውን ፶ (ኀምሳ) አለቃዎች እሳት ከሰማይ አውርዶ አቃጥሏል፤ (፪ኛ ነገ. ፩) በመጐናጸፊያው የዮርዳኖስን ወንዝ ከፍሏል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፬) በእሳት ሠረገላ በዐውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጥቷል፤ (፪ኛ ነገ.፪፥፲፩)፣ በደብረ ታቦር ጌታ ምሥጢረ መንግሥቱን ሲገልጽ ከሙሴ ጋር ዐብሮ ተገኝቷል፤ (ማቴ.፲፯፥፬) ዳግመኛ በመምጣት በሐሳዌ መሲሕ ጊዜ ሰማዕትነትን ይቀበላል፡፡ (ማቴ.፲፯፥፲፩)

የነቢዩ ኤልያስ በረከት ይደርብን!