ብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ

ዲያቆን ዘካርያስ ነገደ
ሐምሌ ፬፤፳፻፲፮ ዓመተ ምሕረት

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አባቶቻችን ሐዋርያትን ሰማዕትነት በተቀበሉበት ቀናት በዓላት ሰይማ ታከብራቸዋለች፡፡ እንዲሁም በስማቸው የተሰየመውን ጾም በመጾም አሠረ ፍኖታቸውን ይከተሉ ዘንድ ምእመናንን ታሳስባለች፡፡ በሐምሌ ፭ ቀን ደግሞ የደጋጎቹን ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳውሎስን በዓል ታደርጋለች፡፡ የእነዚህ ቅዱሳን አባቶቻችን በዓል መደረጉ በአንድ ቀን ሰማዕትነት በመቀበላቸው ነው፡፡

ሁለቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አመራረጣቸው በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ የጥሪው መንገድ ግን ይለያይ ነበር፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ለሐዋርያነት የተመረጠው ጌታችን በገሊላ ባሕር አጠገብ ሲመላለስ ከወንድሙ እንድርያስ ጋር ሆኖ ዓሣ ለማጥመድ መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ወደ እነርሱም ቀርቦ “በኋላዬ ኑና ሰዎችን አጥማጆች እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ” አላቸው፡፡ ወዲያውም መረባቸውን ትተው ተከተሉት፡፡ (ማቴ.፬፥፲፰‐፳)

በአንጻሩ የቅዱስ ጳውሎስ አመራረጥ ደግሞ በተአምር ነው፤ ይኸውም እንዲህ ነው፡፡ በቀደመ ስሙ ሳውል ተብሎ የሚታወቀው ይህ ሐዋርያ የቤተ ክርስቲያን አሳዳጅ ነበር፡፡ ቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ በአይሁድ እጅ ሲወገር የተስማማ የገዳዮቹንም ልብስ ጠባቂ ነበር፡፡ (የሐዋ. ፯፥፶፰-፷)

ቅዱስ መጽሐፍ “ሳውል ግን ቤተ ክርስቲያንን ያፈርስ ነበር ወደ ሁሉም ቤት እየገባ ወንዶችንም ሴቶችንም እየጐተተ ወደ ወህኒ አሳልፎ ይሰጥ ነበር፡፡ . . . ሳውል ግን የጌታን ደቀ መዛሙርት እንዲገድላቸው እየዛተ . . .” እንዲል፡(የሐዋ.፰፥፫፤፱፥፩) በክርስቶስ አምነው የተጠመቁ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ከሊቁ ካህናቱ ዘንድ የፈቃድ ደብዳቤ ጠየቀ፡፡ ይህን ዓላማውን ለማስፈጸም ወደ ደማስቆ ሲጓዝ በርሱ ዙሪያ ከሰማይ መብረቅ ወረደ፤ ዐይኖቹም ታወሩ፤ ወደ ምድርም ወደቀ፡፡

በዚያም ሳለ “ሳውል ሳውል፥ ስለምን ታሳድደኛለህ” የሚለውን ድምፅ ሰማ፡፡ያነጋገረው ሳውል የሚያሳድደው ጌታ ነበር፡፡ “አንተ የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ፤ የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብኻል” አለው፡፡ ከዚያም በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ተነሥቶ ወደ ከተማው ገባ፡፡ ሦስት ቀንም ሳይበላ ሳይጠጣ ተቀመጠ፡፡ ሐናንያ የተባለው ከደቀ መዛሙርት ወገን የሆነ ወደ እርሱ ዘንድ ቀርቦ ጸለየለት፤ ዐይኖቹም ተፈወሱ፤ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ (የሐዋ.፱፥፩‐፲፰)

ቅዱስ ጳውሎስ በወቅቱ ስለሆነው ነገር ለቆሮንቶስ ምእመናን ሲተረክላቸው “ ከሁሉም በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ፡፡ እኔ ከሐዋርያት ሁሉ የማንስ ነኝና፥ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ” እንዲል፡፡ (፩ኛቆሮ.፰፥፱)

የቤተ ሰብ ሕይወታቸው

ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በቤተ ሳይዳ ነው፡፡ ቤተ ሰቦቹ ደግሞ በቅፍርናሆም ይኖሩ ነበር፡፡ የኦሪት መጻሕፍትን ያልተማረ ከዝቅተኛው የማኅበረሰብ ክፍል የተገኘ ሰው ነበር፡፡ (የሐዋ. ፬፥፲፫) ጳውሎስ ደግሞ በኪልቅያ በምትገኘው በጠርሴስ ተወለደ፡፡ ከአይሁድ ወገን ከብንያም ወገን ነበር፡፡ (ፊል.፫፥፭) በጠርሴስም ሳለ በገማልያል እግር ሥር የኦሪት ትምህርቱን ተማረ፤ በትምህርቱም የተመሰከረለት ነበር፤ (የሐዋ.፳፪፥፫፤፳፮፥፳፬) ይህ የሚያሳየው የእግዚአብሔር መንግሥት ለተማሩትም ላልተማሩትም፣ ለባለጸጎችም ለድሆችም የተዘጋጀ መሆኑን ነው፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ ባለ ትዳር ነበር፡፡ አማቱም ታማ በነበር ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤቷ ገብቶ እንደፈወሳት በወንጌል ተጽፏል፡፡ (ማቴ.፰፥፲፬‐፲፭) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ድንግል ነበር፡፡ “ሰው ሁሉ እንደ እኔ ሊሆን እወዳለሁና ነገር ግን፥ እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ለራሱ የጸጋ ስጦታ አለው፥ አንዱ እንደዚህ ሁለተኛውም እንደዚያ፡፡ ላላገቡና ለመበለቶች ግን እላለሁ፡- እንደ እኔ ቢኖሩ ለእነርሱ መልካም ነው፤ ነገር ግን፥ በምኞት ከመቃጠል መጋባት ይሻላልና፥ ራሳቸውን መግዛት ባይችሉ ያግቡ” በማለት ለቆሮንቶስ ምእመናን ጽፏል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፯፥፯‐፱) ቤተ ክርስቲያን እንደ ጴጥሮስ ያገቡ እንደ ጳውሎስ ያሉ ደናግላንን ይዛ የምትገኘው ጌታችን ሁሉንም ወደ እርሱ ስለጠራ ነው፡፡

የስማቸው መለወጥ

ቅዱስ ጴጥሮስ የዮና ልጅ ስምዖን ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ (ዮሐ.፳፩፥፲፭) ነገር ግን ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን “እናንተስ ማን ትሉታላችሁ” ብሎ ሲጠይቃቸው ሐዋርያው ተነሣና፡- “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም ጌታችን “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህ፡፡ እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚችም አለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሏትም” በማለት ጴጥሮስ ብሎ ሰየመው፡፡ (ማቴ.፲፮፥፲፯—፲፰)
ጳውሎስን ደግሞ ጌታችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲጠራው በመጀመሪያ ስሙ ሳውል ብሎ ጠራው፤ በምስክርነቱ ጊዜ ደግሞ “ጳውሎስ ሆይ፥ በኢየሩሳሌም ስለ እኔ እንደ መሰከርህ እንዲሁ በሮሜም ትመሰክርልኝ ዘንድ ይገባሃልና፥ አይዞህ አለው፡፡” (የሐዋ.፳፫፥፲፩)

አገልግሎታቸው

የቅዱስ ጴጥሮስ አገልግሎቱ በአብዛኛው ሕግ ለተጻፈላቸው፣ ነቢያት ለተላኩላቸው፣ መሥዋዕት ለሚያቀርቡ፣ ግርዛት ለተሰጣቸው ለአይሁድ ነበር፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የቅዱስ ጳውሎስ አገልግሎት የነበረው በአሕዛብ መካከል ነበር፡፡ ይህንንም ሲመሰክር “ለተገረዙት ሐዋርያ እንዲሆን ለጴጥሮስ የሠራለት፥ ለእኔ ደግሞ ለአሕዛብ ሐዋርያ እንድሆን ሠርቷልና፡፡” ብሏል፡፡ (ገላ.፪፥፯‐፰) እንዲያውም በአንድ ወቅት ጳውሎስና በርናባስን አይሁድ ትምህርታቸውን በተቃወሟቸው ጊዜ “እነሆ ወደ አሕዛብ ዘወር እንላለን እንዲሁ ጌታ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ለማዳን ትሆን ዘንድ ለአሕዛብ ብርሃን አድርጌሃለሁ ብሎ አዞናልና” ብለው ነበር፡፡ (የሐዋ. ፲፫፥፵፮—፵፯)

በበዓለ ኀምሳ ቅዱሳን አባቶቻችን ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ከተቀበሉ በኋላ ጴጥሮስና ዮሐንስ በትምህርታቸው በኢየሩሳሌም ለነበሩ ነፍሳት ደረሱ፡፡ በአንድ ቀን ብቻ ሦስት ሺህ ነፍሳት ወደ ቤተ ክርስቲያን ተጨመሩ፡፡ (የሐዋ.፪) ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ “ከሁላችሁ ይልቅ በልሳኖች እናገራለሁና እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ” በማለት ስለተሰጠው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ መስክሯል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፲፬፥፲፰) ሁለቱም ሐዋርያት በምእመናን ላይ እጃቸውን በመጫን ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ያሳድሩ ነበር፡፡ (የሐዋ.፰፥፲፬፤፲፱፥፭‐፮)

በአገልግሎታቸው ድንቅ ተአምራትን ፈጽመዋል፡፡ ለምሳሌ ስለ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፡፡ “እግዚአብሔርም በጳውሎስ እጅ የሚያስገርም ተአምራት ያደርግ ነበር፤ ስለዚህም ከአካሉ ጨርቅ ወይም ልብስ ወደ ድውዮች ይወስዱ ነበር፥ ደዌያቸውም ይለቃቸው ነበር ክፉዎች መናፍስትም ይወጡ ነበር፡፡” (የሐዋ.፲፱፥፲፩—፲፪) በኢዮጴም ጣቢታ የምትባል አገልጋይን ከሞተች፤ አጥበውም በሰገነት ከአኖሯት በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ካለበት ተጠርቶ ከጸለየ በኋላ ጣቢታ ሆይ ተነሽ ሲላት ዐይኖቿን እንደከፈተች ተጽፏል፡፡ (የሐዋ.፱፥፴፮—፵፪) በተመሳሳይ ቅዱስ ጳውሎስ አውጤኪስ የሚባል ከሦስተኛ ደርብ ወደ ታች ወድቆ የሞተን ጎልማሳ እንዲነሣ አድርጓል፡፡ (የሐዋ.፳፥፯—፲፪)

መልእክታት

ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት መልእክታትን ለምእመናን ጽፏል፤ ቅዱስ ጳውሎስ በአካል ተገኝቶ ለሰበካቸውና ላጠመቃቸው የሮሜ፣ የቆሮንቶስ፣ የገላትያ፣ የኤፌሶን፣ የፊልጵስዩስ እና የቆላስይስ፣ የተሰሎንቈ፣ ለዕብራውያን ምእመናን መልእክታትን የጻፈ ሲሆን ለመንፈስ ቅዱስ ልጆቹ ለጢሞቴዎስ፣ ለቲቶ እና ለፊልሞና መልእክታትን ሰዶላቸዋል፤ በአጠቃላይ ዐሥራ አራት መልእክታትን ጽፏል፡፡

ሰማዕትነታቸው

ሁለቱም ቅዱሳን ሐዋርያት በሮማው ቄሳር ኔሮን ዘመን ፷፯ ዓ.ም. ሰማዕትነትን ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ቁልቁል ተሰቅሎ ሰማዕትነት የተቀበለ ሲሆን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ አንገቱን ተቀልቶ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡
በረከታቸው ይደርብን፤ አሜን!