በዓለ ግዝረት

ጥር ፭፤፳፻፲፭ ዓመተ ምሕረት

በከበረች በጥር ስድስት ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ ግዝረት በመግባት የኦሪትን ሕግ ፈጸመ፤ ልሳነ ዕፍረት ሐዋርያው ጳውሎስ “ጌታ ክርስቶስ በሥጋው ግዝረትን ተቀበለ፤ ለአባቶች የተሰጠውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ” ብሎ እንደተናገረ።

ለብዙዎችም ጌታችን ወደ ቤተ ግዝረት እንዳልገባና እንዳልተገረዘ ይመስላቸው ነበር፡፡ እነርሱ እንዳሰቡት ሁኖ ቢሆን ኑሮ አይሁድ ታላቅ ምክንያትን የሚያገኙ በሆኑ ነበር፡፡ ጌታችን ግን የግዝረትን ሕግ ፈጸመ፤ ለእኛ በግዝረት ፈንታ የክርስትና ጥምቀትን ሰጠን፤ የፋሲካውንም ቂጣ በላ፤ በእርሱም ፈንታ ሥጋውንና ደሙን ሰጠን።

የከበረ ወንጌል ስምንተኛው ቀን በተፈጸመ ጊዜም ሕፃኑን ሊገዝሩት ወሰዱት፤ ሳትፀንሰው መልአኩ እንዳወጣለት ስሙን ኢየሱስ አሉት እንዳለ ንጽሕት ድንግል እመቤታችን ማርያም ጻድቅ አረጋዊ ዮሴፍን እንደ ሕጉ ልጄን እንዲገርዘውና ስሙንም እንድንሰይመው ብልህ የሆነ ገራዥ ሰው አምጣልኝ አለችው። ዮሴፍም ሔዶ የሚገርዝ ባለሙያ አመጣ፤ ያ ባለሙያም ሕፃኑን ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በእናቱ በንጽሕት ድንግል ማርያም ክንድ ላይ አየው፤ “እንድገርዘው ሕፃኑን በጥንቃቄ ያዙት” አላቸው።

ሕፃን ጌታ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፤ “ባለሙያ ገራዥ ሆይ፥ ደሜ ሳይፈስ ትገርዘኝ ዘንድ ትችላለህን? በዚያች ዕለት ካልሆነ በቀር ደሜ አይፈስምና፤ ጐኔን በጦር ሲወጉኝ ያን ጊዜ ውኃና ደም ይፈሳል፤ ለአዳምና ለሚያምኑ ልጆቹ መድኃኒት ይሆናል።”

የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተናገረውን ያ ባለሙያ በሰማ ጊዜ አደነቀ፤ ዕቃውንም ሰብስቦ ተነሥቶ ከሕፃኑ ጌታ እግር በታች ሰገደ፤ ያንጊዜም ምላጮቹ በእጆቹ ላይ ቀልጠው እንደ ውኃ ሆኑ፤ የከበረች ድንግል እመቤታችንን ማርያምን “ከሴቶች ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ፤ የማኅፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው፤ ይህ ልጅሽ ስለርሱ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት የሕያው አምላክ ልጅ ነው” አላት።

ሕፃኑም ለዚያ ባለሙያ ዳግመኛ መልሶ እንዲህ አለው፤ “እኔ ነኝ፥ ትገዝረኛለህን ወይስ ተውክ? ወይም ያባቶቼ አባቶች እንዳደረጉ እኔ ላድርግ?” ያም ባለሙያ “የአባቶችህ አባቶች እነማን ናቸው?” አለው፤ ሕፃን ጌታችንም “አብርሃም ይስሐቅ ያዕቆብ የሕዝቡ ሁሉ አባቶች የሆኑ ናቸው፤ ለእነርሱም ይህ ግዝረት አስቀድሞ ከአባቴ ዘንድ ተሰጣቸው፤ ባለሙያውም እኔ ከአንተ ጋር እናገር ዘንድ አልችልም፤ በአንተ ህልውና መንፈስ ቅዱስ አለና” አለው።

በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ ጌታችን ዐይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ “አባት ሆይ፥ ለአብርሃም ለይስሐቅ ለያዕቆብ አስቀድሞ ግዝረትን የሰጠሃቸው ያቺን ግዝረት ዛሬ ለእኔ ስጠኝ” አለ። ያን ጊዜ ያለ ሰው እጅ በሕፃኑ ሥጋ ላይ ግዝረት ተገለጠች። ድንግልናዋ ሳይለወጥ ከድንግል ማኅፀን እንደ መውጣቱ የጌታችን ግዝረቱ የማይመረመር ሆነ፤ እንዲሁ ወደ ሐዋርያት በተዘጋ አዳራሽ መግባቱና መውጣቱ እንደማይመረመር እንዲሁ እንደ ፈቀደ ከረቀቀ ጥበቡ ችሎታውን በመገረዝ ከሥጋው ምንም ምን ሳይቆረጥ ገለጠ።

አዳምንና ልጆቹን ያድናቸው ዘንድ በፈቃዱ ከጐኑ በመስቀል ላይ የሚፈሰው ደምና ውኃ ካልሆነ በቀር ብዙም ሆነ ጥቂት ሊሆን አይችልም፤ እርሱ በፈቃዱ ሕጉ እንዲፈጸም አስቀድሞ አዘዘ እንጂ።

ያም ባለሙያው ገራዥ ይህን ተአምር ባየ ጊዜና የሕፃኑንም ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ አደነቀ፤ የክብር ባለቤት ከሆነ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር በታች ሦስት ጊዜ ሰገደና “በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ የእስራኤልም ንጉሥ ነህ” አለው። ከዚህም በኋላ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተአምራቱ ያየውንና የሰማውን እየተናገረ ወደ ቦታው ሔደ።

መጽሐፈ ስንክሳር፤ ጥር ስድስት