በዓለ ክብሩ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ ፲፱ ቀን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ ሠለስቱ ደቂቅን (አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል) ከነደደ እሳት ያዳነበትን መታሰቢያ በዓል በድምቀት ታከብራለች፡፡

ቅዱስ ገብርኤል አብሣሪ መልአክ እንደሆነ ሁሉ ምእመናን እግዚአብሔርን በማምለካቸው ምክንያት ከአላውያን ገዢዎች ከሚደርስባቸው መከራም የሚታደጋቸው መልአክ ነው፡፡ የፋርስ ንጉሥ የነበረው ናብከደነፆር እግዚአብሔር አምላክ ምድሪቱን እና ሕዝቡን ያስተዳድር ዘንድ ቢፈቅድለት በትዕቢት ተሞልቶ “በኃይሌ አደርጋለሁ፣ በማስተዋል ጥበቤም የአሕዛብን ድንበሮች አርቃለሁ፣ ሀብታቸውንም እዘርፋለሁ፣ የሚቀመጡባቸውንም ከተሞች አናውጣለሁ፣ በእጄም ዓለምን ሁሉ እንደ ወፍ ቤት እሰበስባለሁ፣ እንደ ተተወ እንቁላልም እወስዳቸዋለሁ፤ ከእኔም የሚያመልጥ የለም፤ የሚቃወመኝም የለም” ብሎ በመታበይ የወርቅ ጣዖትን አሠርቶ በባቢሎን አውራጃ ቁመቱ ስድሳ ክንድ፣ ወርዱም ስድስት ክንድ የሆነ የወርቅ ምስል አሠርቶ በዱራ ሜዳ ላይ አቆመው፡፡ (ኢሳ. ፲፥፲፫-፲፬፤ ዳን.፫፥፩)፡፡

መኳንንትንና ሹሞቹን እንዲሁም ሕዝቡን አስጠርቶ በዐዋጅ ነጋሪ “ንጉሡ ናቡከደነፆር ላቆመው ለወርቁ ምስል ስገዱ፤ ወድቆም የማይሰግድ በዚያን ጊዜ በሚነድ እሳት እቶን ውስጥ ይጣላል” ሲል ዐዋጅ አስነገረ፡፡ ይህን ዐዋጅ የሰሙ የንጉሥ ሹማምንት ሁሉ ተደፍተው ለወርቁ ምስል ሰገዱ፡፡ ነገር ግን በመካከላቸው አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል ንጉሡ ላቆመው ምስል አልሰገዱም፡፡

ነገር ሠሪዎችም ይህንን ወሬ ለንጉሥ ባደረሱ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ ካስጠራቸው በኋላ “… አምላኬን አለማምለካችሁ ላቆምሁትም ለወርቁ ምስል አለመስገዳችሁ እውነት ነውን?” ሲል ጠየቃቸው፡፡

አናንያ፣ አዛርያ እና ሚሳኤል ግን በንጉሡ ፊት ቆመው “ንጉሥ ሆይ፥ እኛ የምናመልከው አምላክ በሰማይ አለ፡፡ ከሚነድደው ከእቶኑ እሳት ያድነን ዘንድ ይችላል፤ ከእጅህም ያድነናል፡፡ ንጉሥ ሆይ! ይህም ባይሆን አማልእክትህን እንዳናመልክ ላቆምኸውም ለወርቁ ምስል እንዳንሰግድ ዕወቅ” አሉት፡፡ (ዳን.፫፥፬፫-፲፰)፡፡

የንጉሥ ናቡከደነፆር ቁጣ ከፊት ይልቅ እጅግ ነደደ፤ እሳቱንም ሰባት እጥፍ እንዲያቀጣጥሉና እነዚህን ሦስት ብላቴኖች እጅና እግራቸውን አስረው ከእቶን እሳት ውስጥ እንዲጨምሩአቸው አዘዘ፤ ጋሻ ጃግሬዎቹም ፈጥነው ወደሚነደው እሳት ጨመሯቸው፡፡ እግዚአብሔርም የሦስቱን ወጣቶች የእምነት ጽናት ተመለከተ፡፡ በፊቱ የሚቆመውን ባለሟሉን የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤልንም ከመጣባቸው መከራ ይታደጋቸው ዘንድ ላከላቸው፡፡ ቅዱስ ገብርኤልም ከእስራታቸው ፈታቸው፤ እሳቱንም እንደ ውኃ አቀዘቀዘው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅም ከተጣሉበት ሆነው መልአኩን ልኮ ከዚህ እቶን እሳት ያዳናቸውን አምላክ አመሰገኑት፡፡

ንጉሡ ናብከደነፆርም ሠለስቱ ደቂቅ እሳቱ አንዳች ጉዳት ሳያደርስባቸው በእሳት ውስጥ ሲመላለሱ ተመለከተ፡፡ “እነሆ እኔ የተፈቱ በእሳቱም መካከል የሚመላለሱ አራት ሰዎችን በዚያ አያለሁ ምንም የነካቸው የለም፤ የአራተኛውም መልክ የእግዚአብሔርን ልጅ ይመስላል” ብሎ ፊቱን ጸፍቶ አፉንም ከፍቶ እንዲናገር አደረገው፡፡ ሠለስቱ ደቂቅ በእሳቱ ውስጥ ሆነው እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ሰማቸው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ከነደደው እሳት አዳናቸው፡፡ (ዳን. ፫፥፳፬-፳፮)

ናብከደነፆር የተደረገውን ተአምር ተመልክቶ ወደ እሳቱ በመቅረብ ለሦስቱ ብላቴኖች  “እናንተ የልዑል አምላክ ባሪያዎች ሲድራቅ፣ ሚሳቅንና አብደናጎም ኑ ውጡ” ብሎ ተናገራቸው፡፡ (ዳን.፫፥፳፮) እነርሱም እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ወጡ፡፡ መሳፍንቱና ሹማምቶችም የሚያመልኩት አምላካቸው ቅዱስ እግዚአብሔር የሚነደው እሳት ሰውነታቸውን ሳይበላ፣ የራሳቸውም ጸጉር ሳይነካ፣ የእሳቱም ሽታ በላያቸው እንዳልነበረ አዩ፡፡ ንጉሡ ናቡከደነፆርም በሠለስቱ ደቅቅ ፊት ለእግዚአብሔር ሰገደ፡፡ እግዚአብሔርንም እያመሰገነ ሕዝቡን ሁሉ የብላቴኖቹ ሠለስቱ ደቂቅን አምላክ እንዲያመልኩ፤ አናመልክም በሚሉትና የስደብን ነገር በሚናገሩት ላይ ከፍተኛ ቅጣት እንደሚደርስባቸው ዐዋጅ አስነገረ፡፡ ሚሳቅን፣ ሲድራቅና አብደናጎምንም በባቢሎን አውራጃ ውስጥ ሾማቸው፡፡ ከፍ ከፍም አደረጋቸው፡፡

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ልጆቿን ከእነዚህ ብላቴኖች የእምነት ፍሬ ተምረው፣ የመልአኩ ቅዱስ ገብርኤልንም ተራዳኢነት ተረድተው እግዚአብሔርን በማምለክ እንዲጸኑ ታኅሣሥ ፲፱ ቀንን ትዘክራለች፤ በታላቅ ድምቀትም ታከብረዋለች፡፡

የመላእክት አለቃ የቅዱስ ገብርኤል ምልጃና ተራዳኢነት አይለየን፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

በሁለት ወገን የተሳላችሁ ሁኑ!

ዲ/ን ስንታየሁ አለማየሁ

ሰው በእግዚአብሔር አርአያና አምሳል የተፈጠረ፣ ነገር ግን ከሁሉ የሚልቅ ዕፁብ ድንቅ ፍጥረት ነው። ከአፈር መፈጠሩ ሲታይ “ታስበው ዘንድ ሰው ምንድነው?” ፤ በእግዚአብሔር አርአያና አምሳል መፈጠሩ ሲታይ ደግሞ “ከመላእክት ይልቅ በጥቂት አሳነስኸው፤ የክብርና የምስጋና ዘውድ ጫንህለት፥ በእጆችህም ሥራ ላይ ሾምኸው” ማለቱ የእግዚአብሔርን ቸርነት ሁሉን በአግባቡና በሥዓቱ ፈጥሮ የሚገዛ አምላክ መሆኑን ያስገነዝበናል፡፡ (ዕብ. ፪፥፮-፯)

እግዚአብሔር ሰውን በዚህ በሚያስደንቅ ሁኔታ ከ፬ቱ ባሕርያተ ሥጋ (ከአፈር፣ ከነፋስ፣ ከእሳትና ከውኃ) እና ከ ፫ቱ ባሕርያተ ነፍስ (ሕያዊት፣ ለባዊት፣ ነባቢት) ፈጥሮ ፍጥረትን ሁሉ እንዲጠብቅ፣ እንዲገዛ አድርጓል። የሥጋ ባሕርያት እርስ በርሳቸው የሚቃረኑ ቢሆኑም እንኳ በሰው ላይ ተስማምተውና ጸንተው የፈጣሪን ከሀሊነት አሳይተዋል ። ስለዚህም የሰው ልጅ ስንል የነፍስ እና የሥጋ ተዋሕዶ ማለታችን ነው። የሥጋንና የነፍስን ሚዛን አስማምቶና ከኃጢአት ርቆ የሚኖር ሰው እርሱ በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ነው።

በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ በሁለቱም በኩል መሥራትና የታለመለትን ውጤት ማስገኘት ይችላል።  ማለትም መቁረጥ ከሆነ መቁረጥ፣ መጥረብ ከሆነ መጥረብ… ፤ እንዲሁ ሰው ነፍሱንና ሥጋውን በእግዚአብሔር ቃል፣ በመልካም ምግባርና ሃይማኖት በመጠበቅ ከገለጠ እርሱ በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ነው። ምክንያቱም በእምነት የተገለጠ ክርስትና ነፍሳትን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ያደርሳልና።

ነፍሳችን ከእግዚአብሔር ከተቀበለችው አንዱ ጸጋ ዐዋቂነት ነው። በእምነት በጎ ሥራን ለመሥራት ዕውቀት ያስፈልጋል። በእምነት፣ በዕውቀትና በጥበብ እንደ ባለ አእምሮ ከተመላለስን ለዓለም ምሳሌ ሆነን በክብር በጨለማው ውስጥ እናበራለን። ነገር ግን ዕውቀታችንና ጥበባችን ከእግዚአብሔር ከለየን፤ እግዚአብሔር በሐዋርያው ላይ አድሮ እንደ ነገረን “እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱ መጠን እንዲሁ እግዚአብሔር ይህን የማይገባውን ይሠሩ ዘንድ ሰነፍ አእምሮን ሰጣቸው” እንዲል ይገሥጸናል። (ሮሜ. ፩፥፳፰)

በሁለት በኩል መሳል ለምን ያስፈልጋል?

በሁለት በኩል መሳል የሥጋን ባሕርይ ለነፍስ በማስገዛት የእግዘብሔርን ስም በመቀደስ ክብሩን እንዲወርስ ያደርጋል። ሰዎች በሁለት በኩል መሳላቸው ከራስ አልፈው ለሌሎች ነፍስ መዳን ምክንያት ይሆናሉ። እንዴት ቢሉ፡- የእግዚአብሔርን ቃል በማስተማር፣ በመምከር፣   በማሳመን ብዙዎችን ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ይመልሳሉ። ሃይማኖትንና ምግባርን አስተባብረው በርትተው በመሥራትም የተራበ ያበላሉ፣ የተጠማ ያጠጣሉ፣ የታረዘ ያለብሳሉ፣ አልፎ ተርፎም ለብዙዎች አርአያ ይሆናሉ፡፡ ለዚህ ነው ታላቁ አባት ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ “ለራሱ ብቻ የኖረ ሰው አልኖረም ማለት ነው” ያሉት። ሰው በሕይወቱ የእግዚአብሔርን ቃል ከመማር በተጨማሪ የዓለምን ፍልስፍናና ዕውቀት ማወቅ ተገቢ ነው። እንዲህ ሲሆን ለሁሉም በሚገባው ቋንቋ ነገረ እግዚአብሔር አስተምሮ ለመንግሥቱ ያቀርባልና።

“እግዚአብሔር የለም” በሚሉ ሰዎች ፊት እግዚአብሔር መኖሩን እነርሱ በደረሱበት የዕውቀት ልክ ገልጦ ሲመሰክር “ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ” የሚለውን ሽልማት ይጎናጸፋል፡፡ (ማቴ. ፲፥፴፪) በመንግሥቱም እንደ ፀሐይ ደምቆ ያበራል። ሰዎች በመንፈሳዊም ሆነ ዓለማዊ ሕይወታቸው በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ሲሆኑ ተልእኳቸው በስኬት ይታጀባል፤ ከራሳቸው አልፎ ወደ ሌሎችም ይሻገራል። ለዚህ ነው “እናንተ የምድር ጨው ናችሁ” የተባለው ። (ማቴ. ፭፥፲፫)

ጨው ከራሱ አልፎ ለሌላው ጣዕም ይሰጣል፤ አልጫውንም ያጣፍጣል። በሁለት ወገን የተሳለ ሰውም በምግባሩና በሃይማኖቱ ለሌላው የሕይወት መዓዛ ይሆናል “በሚድኑትና በሚጠፉት ዘንድ ለእግዚአብሔር የክርስቶስ መዓዛ ነንና፤ የሞት መዓዛ የሚገባቸው ለሞት፤ የሕይወት መዓዛ የሚገባቸውም ለሕይወት ናቸው” (፪ኛቆሮ ፪፥፲፭) እንዲል። የምድር ጨው (Nacl) የተገነባው ከሁለት መሠረታዊ ንጥረ ነገሮች ማለትም ከሶዲየም(Na) እና ክሎሪን(Cl) ሲሆን ሁለቱም ለብቻቸው  ለሰው ልጅ ጸር ናቸው። ነገር ግን ሁለቱ አንድ ሲሆኑ ከራስ አልፈው ለሌላ ጣዕም ይሆናሉ። ሰውም መንፈሳዊውን እና ዓለማዊው ሕይወቱን አዋሕዶ ሲገኝ በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ይሆናል፡፡ ከራሱ አልፎ በሥጋም በነፍስም ለሌላው ይጠቅማል።  ከሁሉም በላይ እግዚአብሔርን በመፍራት የሕሊናውን ሚዛን ይጠብቃል፡፡ ምክንያቱም “የጥበብ ሁሉ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው”ና፡፡ (መዝ.፻፲፩፥፲)

መንፈሳዊ አገልግሎትን ከትምህርት ጋር እንዴት ማጣጣም ይቻላል?

መንፈሳዊ አገልግሎት በእግዚአብሔር ለተለየ አገልግሎት መመረጥ እንደ መሆኑ መጠን ከትምህርት፣ ከመደበኛ ሥራችን እና ሌሎች ማኅበራዊ ሕይወታችን ጋር አጣጥሞ መጓዝ ያስፈልጋል፡፡ ለአገልግሎት መጠራታችንን ከተረዳን ከሌሎች ተግባራቶቻችን ጋር በጊዜ ለክተንና አስማምተን በዕቅድ ራሳችንን መምራት ይገባል፡፡ “… አሁንም በፊቱ ትቆሙና ታገለግሉት ዘንድ አገልጋዮቹም ትሆኑ ዘንድ እግዚአብሔር መርጧችኋልና ቸል አትበሉ” ሲል እግዚአብሔር በነቢዩ ሕዝቅያስ ላይ አድሮ እንደተናገረ፡፡ (፪ኛ ዜና. ፳፱፥፩-፲፩፤ ማቴ. ፱፥፱) መመረጥ መልካም እንደሆነ ሁሉ ለተመረጡበት አገልግሎት ታምኖ መገኘትና ማገልገል ከአንድ መንፈሳዊ አገልጋይ ይጠበቃል፡፡ ነገር ግን አገልግሎታችን ፍሬ እንዲያፈራ ሌሎች ከምናከናውናቸው ተግባራት ጋር ማስማማት ግድ ይላል፡፡

መንፈሳዊ አገልግሎት የሚከናወነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው፡፡ አገልግሎቱ የመንፈስ ቅዱስ እንጂ የሰው አለመሆኑን ማመን ተገቢ ነው። በሰው ጥበብ፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ረዳትነት፣ ዕውቀትና ብቃት ብቻ የሚከናወን አይደለም፡፡ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ስንጠይቅ መንፈሳዊው አገልግሎት ብቻ ሳይሆን ለሕይወታችን ለሚያስፈልጉን ነገሮች ሁሉ መቃናት ወሳኝ ነው፡፡ “ካለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም” ብሎናልና፡፡ (ዮሐ. ፲፭፥፭) ስለዚህ የምናከናውናቸውን ተግባራት በጊዜ ለክተንና መድበን ሁሉንም በአግባቡና በሥርዓት ማስኬድ ይጠበቅብናል፡፡ በተለይም ወጣቶች ይህንን ከተረዱ በመልካም አገልግሎታቸው እና ልዩ ልዩ ተግባራት  ለሌሎች አርአያ መሆን እንችላሉ፡፡

ወጣትንነትን ስንመለከት የእሳትነት ዘመን እንደ መሆኑ መጠን ስሜታዊነት ጎልቶ የሚታይበት ጊዜ ነው፡፡ በተለይም በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ውስጥ አገልግሎትን ከመደበኛ ትምህርት ጋር አጣጥሞ መጓዝ ላይ በርካታ ችግሮች ይስተዋላሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዱ ራስን በዕቅድ አለመምራት ነው፡፡ ዕቅድ ሲታቀድ ደግሞ በጊዜ ተለክቶ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ ቁርጠኛ መሆንን ይጠይቃል፡፡ በተለይም በበርካታ ወጣቶች ላይ የሚታየውን ስሜታዊነት ማረቅ የሚቻለውና ለተጠሩለት አገልግሎት እንዲሁም ለመደበኛ ትምህርት አስፈላጊውን ጊዜ ሲሰጡ   ነው፡፡

በመጀመሪያ የሚያስፈልጉትንና የማያስፈልጉትን መለየት ይገባል። ቀጥሎም አሁን

ከሚያስፈልገው በመነሣት ሁሉንም በቅደም ተከተል መዘርዘር ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም፡-  ጊዜ የሚባል በጣም ውድ የእግዚአብሔር ስጦታ አለና። ጊዜ በአግባቡ ከተጠቀምንበት ወርቅ ነው፡፡ ለሁሉም ጊዜው አለውና “ለሁሉ ዘመን አለው፤ ከፀሐይ በታችም   ለሆነ ነገር ሁሉ ጊዜ አለው፡፡” (መክ. ፫፥፩) እንዲል ጠቢቡ፡፡ ጊዜ የለኝም! ነገ አገለግላለሁ!  ነገ እሠራለሁ! ማለት ለተጠሩለት አገልግሎት ታማኝ ሆኖ አለመገኘትን ያመለክታልና ምክንያት ከመደርደር ይልቅ በተገቢ ጊዜና ሰዓት ተገቢውን አገልግልሎት መፈጸም ይገባል፡፡ በምንም ጊዜና ሁኔታ ውስጥ ብንሆን እንኳን ሁሉን በተገቢው መንገድ አቀናጅተን እንሠራለን፤ እናገለግላለን፡፡ በሐዋርያው ቃልም እንዲህ እንላለን” … አገልግሎት ስላለን አንታክትም” (፪ቆሮ. ፬፥፩)፡፡

እዚህ ላይ ቆም ብለን ራሳችንን አንድ ነገር እንጠይቅ፡- ጊዜ የሚያንሰኝ ለምንድነው? ለትምህርቴስ? ለአገልግሎቴ ለጓደኞቼ የምሰጠው ጊዜ ምን ያህል ነው? ለቤተሰቦቼስ? ለማኅበራዊ ሚዲያስ? … በአጠቃላይ ምን ምን እያከነወንኩ ነው ጊዜዬን የምጨርሰው? በእውኑ ለአገልግሎት ጊዜ የለኝምን? እነዚህን ጥያቄዎች መመለስ ያስፈልጋል፡፡ ከመለስን

የሚጠቅመንና የሚጎዳንን ከለየን በኋላ ሁሉን በጊዜው እንሥራ፤ “የሚሻለውን ሥራ

እንድትመረምሩና እንድትፈትኑ ክርስቶስ በሚመጣበት ቀን ያለ እንቅፋት ቅዱሳን ትሆኑ   ዘንድ” (ፊል.1፩፥፲) እንዲል፡፡ የሚጠቅመንን ማድረግ ስንጀምር ዕለት ዕለት ያለመታከት

በአግባቡ ካጠናን የሚጠበቅብንን ሁሉ በሰዓቱ ካከናወንን ጊዜ በምንም ሁኔታ ሊያጥረን

አይችልም። በተለይም ደግሞ ተማሪዎች   አንዱ ለእግዚአብሔር የምናቀርበው አሥራታችን

ጊዜ ነው። በዚህ ታምነን ከተገኘን ለነፍሳችን ስንቅ ለሥጋችን ስኬትን እናገኛለን።

በሚገባ ጊዜያችንን ተጠቅመን ትምህርታችንን ከተማርንና እርሱን ካገለገልን በማያልቅ በረከት ይባርከናል፤ በሁለት ወገን የተሳልን ሰይፎች ሆነንም እንወጣለን፡፡

አምላከ ቅዱሳን ለተጠራንበት አገልግሎት ታምነን በሥጋም በነፍስም ተባርከን ስሙን ለመቀደስ መንግሥቱንም ለመውረስ ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በኣታ ለማርያም

ታኅሣሥ ሦስት በዚህች ቀን አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሦስት ዓመት ሲሆናት ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ነው፡፡ እርሷ ለእግዚአብሔር የስእለት ልጅ ነበረችና፡፡

እናቷ ቅድስት ሐና ልጅ የሌላት ስለሆነች በቤተ እግዚአብሔር ውስጥ ከሴቶች ተለይታ ርቃ ትኖር ነበር፡፡ ሽማግሌ ከሆነ ከኢያቄም ከባሏ ጋርም እጅግ የምታዝን ሆነች፡፡ እግዚአብሔርም ሐዘናቸውን ሰማ፤ ቅድስት ሐናም እንዲህ ብላ ለእግዚአብሔር ተሳለች፡፡ “የሰጠኸኝን ፍሬ ለእግዚአብሔር አገልጋይ አደርገዋለሁ፡፡”

ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምንም በወለደቻት ጊዜ ሦስት ዓመት በቤቷ ውስጥ አሳደገቻት፡፡ ከዚህም በኋላ ከደናግል ትኖር ዘንድ ወደ ቤተ መቅደስ ወሰደቻት፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ስለ ምግቧ በመጨነቁ ሕዝቡን ሰብስቦ ሳለ መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፤ ዘካርያስ ለእርሱ የመጣ ሀብት መስሎት ታጥቆ እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ ከስምዖን ጀምሮ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም በተራ ቢሞክሩ በተመሳሳይ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ ብለው ሐና እና ኢያቄም እንዲቀርቡ አደረጓቸው፤ ለእነርሱም ራቀባቸው፤ ዘካርያስም ሐናን እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ ባላት ጊዜ ቅድስት ድንግል ማርያም ድክ ድክ እያለች እናቷን ስትከተል መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መግቧት ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱም ሕዝቡም የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር ብለው አስገቧት፤ ይህም ታኅሣሥ ፫ ቀን ነበር፡፡

በቤተ መቅደስም ምግቧን ከመላእክት እየተቀበለች አሥራ ሁለት ዓመት ኖረች፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ወደ ዓለም መጥቶ ከእርሷ ሥጋን እስከነሣ ድረስ፡፡

ከሴቶች ሁሉ የተመረጠች ይህቺ ናት፤ በቤተ መቅደስም በመኖር አሥራ ሁለት ዓመት ሲፈጸምላት እርሷ ለእግዚአብሔር የተሰጠች የስእለት ልጅ ናትና ለሚጠብቃት ይሰጧት ዘንድ ካህናት እርስ በእርሳቸው ተማከሩ፡፡ በሴቶች ላይ የሚደርስ በእርሷ ላይም ይደርስባታል ብለው ስለፈሩ በቤተ መቅደስ ውስጥ ይተዋት ዘንድ ለእነርሱ ትክክል መስሎ አልታያቸውም፡፡ ስለዚህም ሊጠብቃት ለሚገባው በእርሷ ላይ እጮ ለያኖሩ ወደዱ፡፡

ከዚህም አስቀድሞ ሊቀ ካህናት ዘካርያስ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን “ልጄ ማርያም ሆይ አንቺ እንዳደግሽና ለአካለ መጠን እንደደረስሽ ዕወቂ፤ ልትታጨ ትወጃለሽን? እግዚአብሔርን የሚፈራ መልካም የሆነ የተባረከ ጎልማሳ እንፈልግልሽን? ወይም በሕይወትሽ ዘመን ሁሉ በቤተ መቅደስ ተቀምጠሽ እግዚአብሔርን ልታገለግዪው የምትሺ ከሆነ በሴቶች ላይ የሚደርሰው በሚደርስብሽ ወራት ወደ ቤተ መቅደስ ደጅ ከመግባት ትጠበቂ ዘንድ በኦሪቱ የተፈጸመውን የርግማን ሥርዓት በአንቺ ላይ እንሠራለን” አላት፡፡

ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም “እነሆ እኔ የእግዚአብሔር አገልጋዩ በፊታችሁ ነኝ፤ አባትና እናት የሉኝም፤ ስሙ ቡሩክ ምስጉን ከሆነ ከእግዚአብሔር በታች ከእናትና አባት ፈንታ እናንት ናችሁና የእግዚአብሔር ትእዛዝ እንደምታውቁ አድርጉ” ብላ መለሰች፡፡

ካህናቱና ማኅበሩም ሁሉ ዘካርያስን ወደ ቤተ መቅደስ ገብተህ ስለዚህች ብላቴና ማርያም ወደ እግዚአብሔር ጸልይ አሉት፡፡ ዘካርያስም ገብቶ ሲጸልይ በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና እንዲህ አለው፡- “ዘካርያስ ሆይ ወጥተህ ከዳዊት ወገን ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን ሁሉ ወንዶች ሰብስብ፤ የእያንዳንዱንም በትር ከስሙ ጋር ውሰድ፡፡ ወደ ቤተ መቅደስም በምሽት ገብተህ ወደ እግዚአብሔር ጸልይበት፡፡ በነጋ ጊዜም በትሮቻቸውን አውጣ፡፡ እግዚአብሔርም በበትሩ ላይ ምልክት ለገለጠልህ ለዚያ ሰው ማርያምን ተቀብሎ ሊጠብቃት ይገባዋል፡፡”

ካህኑ ዘካርያስም ወጥቶ አንድነት ለተሰበሰቡት ሕዝብ የእግዚአብሔር መልአክ የነገረውን ነገራቸው፡፡ በዚያንም ጊዜ “ከዳዊት ወገን ጎልማሳም ቢሆን ሽማግሌም ቢሆን ሚስቱ የሞተችበት ሁሉ በኢየሩሳሌም ወደ አለ ቤተ መቅደስ ይሂድ” እያሉ ዐዋጅን ዙረው የሚናገሩ በእስራኤል አገር ሁሉ ላከ፡፡

ከዳዊት ወገን የሆነ ጠራቢው ዮሴፍም በሰማ ጊዜ በትሩን ይዞ ከናዝሬት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ፡፡ ካህኑ ዘካርያስም የሁሉንም በትሮች ተቀብሎ ስማቸውን በላያቸው ጻፈ፡፡ ቁጥራቸውም አንድ ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አምስት በትሮችን ወደ ቤተ መቅደስ አስገብቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ እንዲሁም ሰዎች ሁሉ ከቤተ መቅደስ ውጪ ቆመው ይጸልዩ ነበር፡፡ ዘካርያስም ጸሎቱን በፈጸመ ጊዜ በማግስቱ  ለእያንዳንዱ በትራቸውን አውጥቶ ሰጠ፡፡ ጠራቢው ዮሴፍም በትሩን ሊቀበል በቀረበ ጊዜ የዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩም ጫፍ ላይ ኦ ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት” የሚል ጽሑፍ አገኙ፤ ርግብም እየበረረች መጥታ በአረጋዊው ዮሴፍ ራስ ላይ አርፋለች፤ ካህናቱና ሕዝቡም ሁሉ አይተው እጅግ አደነቁ፤ ምስጉን የሆነ እግዚአብሔርምን አመሰገኑት፡፡

ዘካርያስም ዮሴፍን “ዮሴፍ ሆይ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ እንደተናገረ ድንግል ማርያምን ወደ ቤትህ ወስደህ ጠብቃት” አለው፡፡ የሴፍም ቅድስት ድንግል ማርያምን ከካህናት እጅ ተቀበላት፣ በእርሱም ዘንድ ኖረች፡፡ ከዚህም በኋላ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ስለ እግዚአብሔር ልጅ ከእርሷ ሰው ሁኖ ስለመወለዱ በዮሴፍ ቤት አበሠራት፡፡

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቃል ኪዳንና በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስንክሳር ታኅሣሥ ፫ ቀን

ወጣትነት እና እጮኝነት

በዲ/ን ኢያሱ መስፍን

 ክፍል ሦስት

የእጮኝነት ጊዜ

ተገቢውን ዝግጅት እና ጥንቃቄ አድርጎ እጮኛውን የመረጠ ሰው እስከሚያገባበት ቀን ድረስ እጮኛ መሆኑ የሚሰጠው ብዙ የተለየ መብት አይኖርም። የትዳር ተስፋ ያላቸው ከመሆኑ ባሻገር ከልብ ጓደኛና፣ የተለየ አካላዊ ግንኙነት እንዲኖራቸው ለእጮኛሞች አይፈቀድም። ከጋብቻ በፊት የሚደረግ ሩካቤ ዝሙት ነው። ሩካቤ ሳይፈጸም ጾታዊ ደስታን ለማግኘት የሚፈጸሙ እንደ መሳሳም፣ መተቃቀፍ፣ መነካካት ያሉ ድርጊቶች መጽሐፍ ቅዱስ መዳራት ብሎ የሚጠራቸውና ያልተፈቀዱ የኃጢአት ሥራዎች ናቸው። መጽሐፍ ቅዱስ ይዞ መማማል፣ በንስሓ አባቶች ፊት ቃል መገባባት፣ ያለ ቤተ ክርስቲያን ዕውቅና አብሮ ሄዶ መቁረብ፣ ያለ ቤተ ክርስቲያን ዕውቅና ቀለበት መተሳሰር እና የመሳሰሉት ድርጊቶች እጮኛሞች አካላዊ ግንኙነት እንዲኖራቸው መብት የሚሰጡ አይደሉም። መሓላ በራሱ ኃጢአት ከመሆኑም በተጨማሪ (ማቴ 5፡34) ጋብቻን ሊተካ የሚችል አይደለም። አንዳንድ ንስሓ አባቶች ልጆቻቸው አንዳቸው ሌላኛውን እንዳይበድሉ በማሰብ እርሳቸው ባሉበት ቃል እንዲገባቡ የሚያደርጉ ሲሆን ይህ የማይበረታታ እና ብዙ ችግር ይዞ ሊመጣ የሚችል ድርጊት ነው። አንደኛ ይህንን ቃል እንደ ጋብቻ ቆጥረው ወደ ሩካቤ የሚገቡ ጥንዶች ይኖራሉ፡፡

እንዲሁም እጮኝነት የትውውቅ ጊዜ እንደመሆኑ የእጮኞቻቸውን ክፉ አልያም ሊሻሻል የማይችል እና ከነርሱ ፈቃድ ጋር የማይሄድ ነገር ያዩ ሰዎች ሐሳባቸውን እንዳይቀይሩና ተገቢውን ጥንቃቄ እንዳያደርጉ የገቡት ቃል የሚያስጨንቅ እስራት ይሆንባቸዋል። ይህን እና ይህን የመሰለውን ፈተና ይዞ ስለሚመጣ ቤተ ክርስቲያን በሠርጋችን ዕለት ቃል እስክታስገባን ድረስ እንደዚህ ዓይነት ቃል ኪዳኖች ውስጥ ላለመግባት መጠንቀቅ ያስፈልጋል። በንስሓ አባቶች ግፊት የምንገባ ከሆነ ያ ቃል ኪዳን አጋራችንን ላለመበደል እና ክፉ ላለማድረግ የገባነው እንጂ የጋብቻ እንዳልሆነ ማወቅ ያስፈልጋል። ከትዳር በፊት ሩካቤን እና አብሮ መኖርን የሚያበረታቱ ንስሓ አባቶችንም እንቢ ማለት ነውር አይደለም። ቤተ ክርስቲያን በሰው እና በእግዚአብሔር ፊት ዐውጃ፣ ተገቢውን ጸሎት አድርጋ በጋራ እስካላቆረበችን ድረስ ተስማምቶ መቁረብ፣ በአንድ ቀን መቁረብ እንጂ አብሮ መቁረብ ሊባል አይችልም። የዚያን ቀን ከእኛ ጋር ተሰልፈው ከቆረቡት ሰዎች የተለየ አንዳንች ኅብረት አይኖረንም ስለዚህ ይህም ጋብቻን የሚተካ ድርጊት አይደለም።  ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሰርጉ ቀን በቅብዓ ሜሮን አክብራ ከምታደርገው ቀለበት ውጪ  ሌላ የቀለበት ሥርዓት የላትም፡፡ ስለዚህ በግል አልያም ቤተሰብ ባለበት የሚደረግ ቀለበት የመደራረግ ሥርዓት መንፈሳዊውን ጋብቻ የሚተካ ስላልሆነ የተለየ መብት አይሰጥም።

ስለዚህ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች በዝሙት ፈተና ወድቀው እግዚአብሔርን እንዳያሳዝኑ ለዚህ ፈተና ከሚዳርጉ ሁኔታዎች ራሳቸውን አርቀው ከዝሙት በመሸሸ (1ቆሮ 6፣18) አካላቸውን እና ሐሳባቸውን በመቀደስ፣ በጋራ ቃለ እግዚአብሔርን በመማር፣ ምክረ ካህን በመቀበል፣ የንስሓ እና የቅዱስ ቁርባን ሕይወትን በመለማመድ የእጮኝነት ጊዜያቸውን ሊያሳልፉ ይገባል።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ወጣትነት እና እጮኝነት

በዲ/ን ኢያሱ መስፍን

 ክፍል ሁለት

እጮኝነት ከማን ጋር?

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለዚህ ጥያቄ የምትሰጠውን መልስ አለመረዳት በሥጋም በነፍስም ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል ስሕተት ውስጥ ሊያስገባ ይችላል። የትዳር አጋር አልያም እጮኛ ለመምረጥ የሃይማኖት አንድነት፣ ዝምድና፣ ዕድሜ፣ ወዘተ ያሉት  ቅድሚያ የምንሰጣቸው መሥፈርቶች በመሆናቸው ትልቅ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል። ያስቀደምናቸው መሥፈርቶች ጊዜያዊ እና ሥጋዊ ብቻ ከሆኑ ግን የጋብቻን መንፈሳዊ ዓላማ ለማሳካት እንቅፋት ከመሆናቸውም ባሻገር እስከ ፍጽሜ የሚጸና ጥምረት ለመፍጠርም አዳጋች ይሆናሉ። ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ልጆቿ ቅድሚያ እንዲሰጧቸው አጥብቃ ከምታዝዛቸው መሥፈርቶች መካከል ሃይማኖት እና መንፈሳዊ ሕይወት የመጀመሪያዎቹ ናቸው።

በብሉይ ኪዳንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን በሃይማኖት ከማይመስሉን ሰዎች ጋር በትዳር መጣመር የተነቀፈ ምግባር ነው፡፡ አብርሃም ለልጁ ይስሐቅ ሚስትን ፍለጋ ሎሌውን ሲልክ ከአሕዛብ እና ከከነዓናውያን እንዳያጋባው አስምሎ እግዚአብሔርን ከሚያውቁ ከዘመዶቹ አገር ሚስት እንዲያመጣለት የላከው በዚሁ ምክንያት ነው። (ዘፍ 24) እንዲህ ዓይነት ታሪኮችን በመጽሐፍ ቅዱስ ማግኘት የተለመደ ነው። በሐዲስ ኪዳን ያለን አማኞችም ከማይመስሉን ሰዎች ጋር የሚኖረንን ግንኙነት በተመለከተ ጥብቅ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶናል። “ከማያምኑ ጋር በማይሆን አካሔድ አትጠመዱ፤ ጽድቅ ከዐመፅ ጋር ምን ተካፋይነት አለውና? ብርሃንም ከጨለማ ጋር ምን ኅብረት አለውና?” (2ቆሮ6፡14)። እስከ ሕይወት ፍጻሜ ከሚቀጥል በመንፈስ ብቻ ሳይሆን በአካል አንድ ከሚያደርግ ከጋብቻ በላይ ልንጠነቀቅለት የሚገባ አካሔድ ወይም ጉዞ ምን አለ?

ብዙዎች ለዚህ ስሑት ሐሳብ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃ አድርገው የሚያቀርቡት አንድ ጥቅስ አለ፡፡ ይህም ቅዱስ ጳውሎስ “ሌሎችንም እኔ እላለሁ ጌታ አይደለም፣ ከወንድሞች ወገን ያላመነች ሚስት ያለችው ቢኖር እርስዋም ከእርሱ ጋር ልትቀመጥ ብትስማማ አይተዋት…” የሚለው ነው፡፡ (1ቆሮ. ፯፥፲፪) የገዛ ፈቃዱን ለማስፈጸም ሳይሆን የእግዚአብሔርን ቃል በእውነት ለመረዳት ለሚያስብ ሰው ይህ ኃይለ ቃል ካላመኑ ሰዎች ጋር ለመጋባት መብት የሚሰጥ አይደለም። ቅዱስ ጳውሎስ “የማታምን ሴት ለማግባት የፈለገ ሰው ቢኖር” ብሎ አላስተማረም፤ ይልቁንም  ክርስትና ባልተስፋፋበት በዚያ ዘመን ተጋብተው ከሚኖሩ መካከል ባል ወይ ሚስት በወንጌሉ ቢያምኑ የትዳር አጋሬ አላመነም ብለው የገነቡትን ቤት እንዳያፈርሱ ልጆች እንዳይበተኑ እና ክርስትና የጸብ እና የመለያየት ምክንያት እንዳይሆን የተሰጠ ትእዛዝ ነው። መልእክቱ አግብተው የሚኖሩትን እንጂ ገና ያላገቡትን አይመለከትም።

ሐዋርያው ዝቅ ብሎ ይህ ያላመነ አጋር ለማመን አልያም ከክርስቲያን አጋሩ ጋር አብሮ ለመኖር ፈቃደኛ ባይሆን መተው ወይም መፍታት እንደሚቻል በመናገር ጌታችን ከዝሙት ውጭ አትፋቱ ብሎ ካስቀመጠው ሥርዓት በተጨማሪ የሃይማኖት ልዩነት ሌላ ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ገልጿል። እጮኛ የሚይዝ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት እየመረጠ ያለው የትዳር አጋሩን በመሆኑ እና ከጋብቻ ውጪም እጮኛ የሚያዝበት ሌላ አንዳች ዓላማ ስለማይኖረው እስካልተጋባን ምን ችግር አለው ሊል አይችልም።

ከማያምኑ ጋር ብንጋባ ችግሩ ምንድን ነው?

ቅዱሳት መጻሕፍት እንዳዘዙን ቢቻለንስ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ልንኖር ይገባናል (ሮሜ. ፲፪፥፲፰)። ይህ ማለት ግን ጥላቻን እና አለመግባባትን ማስወገድ መቻል ማለት እንጂ ትዳርን በሚያህል የተቀደሰ ትስስር ወስጥ መግባት ማለት አይደለም። የተቀደሰውን ለውሾች እንዳንሰጥ ጌታችን አስጠንቅቆናል (ማቴ 7፡6)። በክርስቶስ ኢየሱስ ደም የከበረ ከውኃ እና ከመንፈስ ተወልዶ የሥላሴን ልጅነት ያገኘ እና የእግዚአብሔር መቅደስ ተብሎ የተጠራ ሰውነታችን የተቀደሰ አይደለምን?  ይህንን ሳናስተውል ቀርተን በእምነት የማይመስለን እጮኛ ብንይዝ ከሚገጥሙን እንከኖች መካከል የተወሰኑትን እናንሣ።

. የትዳርን ዓላማ ማሳካት አንችልም

ክርስቲያኖች ወደ ምንኩስናም ሆነ ወደ ጋብቻ የሚገቡበት ዓላማ አንድ ዓይነት ነው። እርሱም ቅድስና! የድንግልናን ሕይወት የመረጠ ሰው ራስን መግዛትን ገንዘብ አድርጎ ፍትወታቱን ለፈቃደ ነፍሱ አስገዝቶ ለመኖር እንደሚችል አምኖና ወስኖ ነው። የዚህ ጉዞ ዓላማውም ኃጢአትን አሸንፎ በምድር መላእክትን መስሎ መኖር ነው። በሌላ በኩል ራስን መግዛትን እና ድንግልናን መጠበቅን ገንዘብ ማድረግ ያልቻለ ሰው ስለ ዝሙት ጠንቅ እንዲያገባ ተፈቅዶለታል (1ቆሮ 7፡2)። የዚህም ሰው ጉዞ በዝሙት ተፈትኖ ሳይወድቅ በትዳር ንጽሕናውን ጠብቆ የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረስ ነው። ስለዚህም የትዳር አንዱ ዓላማ መረዳዳት ነው። መረዳዳት ማለትም ብዙዎች እንደሚያስቡት በሥራ እና በኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን በዋናነት በመንፈሳዊ ሕይወት ነው። ጠቢቡ ሰሎሞን “አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን ይሻላል ቢወድቁ አንዱ ሁለተኛውን ያነሣዋልና” (መክ 4፡9) እንዳለ አንዱ ወድቆ ከእግዚአብሔር መንግሥት እንዳይርቅ ሌላኛው አጋዥ ሊሆነው፣ ቢዝል ሊያበረታው፣ ተስፋ ቢቆርጥ ሊያጽናናው ይችላልና ተረዳድተው እና ተደጋግፈው የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረስ የትዳር ዋነኛ ዓላማ ነው። ለዚህም ነው ምዕራባውያን ሊቃውንት “the goal of marriage is not happiness; it is holiness” “የጋብቻ ግቡ ደስታ፣ ተድላ አይደለም ቅድስና ነው” የሚሉት።

የማያምን የትዳር አጋር ያለው ሰው ይህንን ዓላማ ሊያሳካ አይቻለውም። ከማያምን ሰው ጋር ተረዳድቶ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በጋራ መግባት የማይሆን ነገር ነው ምክንያቱም ጌታችን እንዳለ “የማያምን ሰው በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል” (ዮሐ 3፡18)። ከማያምኑ ጋር መኖር ለመንፈሳዊ ዝለት መንስኤ እንጂ መፍትሔ ሊሆን አይችልም። ስለዚህ ጋብቻችን እንኳ እጅግ መልካም ቢሆን ከተድላ ሥጋ ያለፈ ለነፍሳችን የሚረባ ነገር አይኖረውም። ክርስቲያኖች ደግሞ እንኳን እንዲህ ያለውን ትልቅ ነገር ቀርቶ ጥቃቅኑን ጉዳይ እንኳ የእግዚአብሔርን ፍቅር እያሰብን ለእርሱ እንድናደርገው ታዝዘናል። “መብላትም ቢሆን መጠጣትም ቢሆን ማንኛውንም ነገር ስታደርጉ ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” (1ቆሮ 10፡31) እንዳለ።

. በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ ያለው ኦርቶዶክሳዊ ጋብቻ መፈጸም አንችልም

ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ልጆቿን በእግዚአብሔር እና በሰዎች ፊት በክብር የምትድርበት ሥርዓተ ተክሊል የሚባል የጋብቻ ሥርዓት አላት። ለደናግል በሚደረገው የተክሊል ጋብቻም ሆነ ለመዓስባን (ደግመው ለሚያገቡ አልያም ድንግልናቸውን ላጡ) ሰዎች በምታደርገው የመዓስባን ጋብቻ (የቁርባን ጋብቻ) መሳተፍ የሚችሉት ምሥጢራተ ቤተክርስቲያንን መፈጸም የተፈቀደላቸው፣ ልጅነትን ያገኙ ክርስቲያኖች ብቻ ናቸው። እግዚአብሔር አምላክ የሚቀበለው ጋብቻ እርሱ ምስክር ሆኖ የተጠራበትን ቅዱስ ጳውሎስ “ሁሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት” እንዳለ እርሱ የሚከብርበትን ጋብቻ ብቻ ነው።

የሰው ልጅ የእግዚአብሔር መንፈስ አልያም የጠላት ዲያብሎስ መንፈስ ያድርበታል። እስራኤል የያዕቆብ አምላክ፣ የእግዚአብሔር ማደሪያ (ሐዋ.፯፥፲፮) እንደ ተባሉ ሁሉ ባቢሎናውያን ደግሞ የአጋንንት ማደሪያ ተብለው ተጠርተዋል (ራእ. ፲፰፥፪)። እያንዳንዱ ሰው የሚያድርበትን መንፈስ የሚመርጠው ራሱ ነው። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን የሚያቀርብ ሥራ እና ምግባር ያለው ሰው የእግዚአብሔር ማደሪያ ይሆናል፡፡ ሐሳቡን እና ድርጊቱን ያልቀደሰ ሰው ደግሞ ለጠላት ማደሪያነት እንደ ተወለወለ ቤት ራሱን ያዘጋጃል (ሉቃ. ፲፩፥፳፭)። በሠርጋችን ቀን የሚኖረን ምግባር በዕለቱ የምንጠራውን የክብር እንግዳ የሚጋብዝ ነው። ወዳጄ ሆይ! በሰርግዎት ቀን የትኛው መንፈስ እንዲገኝ ይሆን የሚፈልጉት? ማንም ጤነኛ አእምሮ ያለው ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ቅዱስ መንፈስ ውጭ ሌላ መልስ እንደሌለው ግልጥ ነው። እግዚአብሔር በማይከብርበት ብዙ መብላት፣ ብዙ መጠጣት፣ ዘፈን፣ ጭፈራ፣ መዳራት እና የመሳሰሉት ኃጢአቶች ባሉበት ቦታ እግዚአብሔር በረድኤት አይገኝም። ኃጢአት የደስታው ምንጭ የሆነለት ዲያብሎስ ግን ሳይጠራ የሚመጣበት ዓለሙ ነው። እነዚህ ሁሉ ኃጢአቶች ባይኖሩ እንኳ ስለ እግዚአብሔር ክብር እንደ እርሱ ፈቃድ አልተደረገምና እግዚአብሔር አይገኝበትም።

በተቃራኒው ቤተ ክርስቲያን በአምልኮተ እግዚአብሔር በሚደረግ ጋብቻ ላይ ጌታችን እንደ ቃና ዘገሊላ ቤት ይገኝበታል። ዛሬም ሠርጉ በሚደረግበት ቤተ ክርስቲያን በሚፈጸመው ቅዳሴ ላይ የጌታችን እውነተኛ ሥጋው እና ደሙን በቤተ ክርስቲያን  ይቀበላሉ፡፡ በዚህ የቅዳሴ ጸሎት ቅዱሳንም በሠርጋችን ይገኛሉ። ንጉሣቸው ባለበት ሁሉ የማይታጡ ሠራዊተ መላእክት ባሉበት መሞሸር የማይፈልግ ማነው? ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን በመሰለ ጋብቻ እንዳንከብር ከምትከለክልባቸው ምክንያቶች አንዱ ከማያምኑ ጋር የሚደረግ ጋብቻ ነው።

. በልጆች አስተዳደግ ላይ አሉታዊ ተጽእኖ አለው 

ከላይ የዘረዘርናቸው መንፈሳዊ ጉዳዮች አያሳስቡኝም የሚል እንኳ ቢኖር የተለያየ እምነት ያላቸው ሰዎች የሚፈጽሙት ጋብቻ ይዞት የሚመጣው ማኅበራዊ ቀውስ ብዙ ነው። ከእነዚህም ወስጥ የልጆች አስተዳደግ ትልቁን ድርሻ ይወስዳል። ወላጆች ልጆቻቸውን ወደየራሳቸው እምነት ለመሳብ የሚያደርጉት ጥረት የልጆችን አእምሮ በብዙ መልኩ የሚጎዳ ሲሆን ይህንን ጉዳት ለመሸሽ ልጆችን ወደ እምነት ተቋማት አለመውሰድ ደግሞ የባሰ ፈጣሪን የማያውቁ እና ከአምልኮተ እግዚአብሔር የራቁ ሆነው እንዲያድጉ ያደርጋል። ሌላኛው ወላጅ ባይቃወምና ልጆች አማኝ ሆነው ቢያድጉ እንኳ ከወላጆቻቸው አንዱ ለእግዚአብሔር መንግሥት ያልታጨ ለዘላለም ፍርድ የተጋለጠ መሆኑን እያሰቡ እንዲኖሩ ይገደዳሉ።

እነዚህና መሰል ጉዳዮች በእምነት ከማይመስሉን ሰዎች ጋር በዚህ መልኩ መጠመድ እንደማይገባን የሚያሳስቡ ናቸው። ከዚህም ባሻገር በአንድ ሃይማኖት ጥላ ሥር መጠለል ብቻውን በትዳር ለመጣመር በቂ ምክንያት አይደለም። ምንም እንኳ በእምነት የሚመስሉንን ሰዎች እንዳናገባ ክልከላ ባይኖርብንም መምህራችን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ የተፈቀዱልን ነገሮች ሁሉ የሚጠቅሙን እና የሚያንጹን አይደሉም (፩ቆሮ. ፮፥፲፪ እና ፩ቆሮ. ፲፥፳፫)። ዓላማቸው ከዓላማችን፣ ፈቃዳቸው ከፈቃዳችን መግጠሙን ማስተዋል ያስፈልጋል። በሃይማኖት እንመሳሰላለን ካልን በኋላ አንዳችን ለፈቃደ እግዚአብሔር መገዛትን ስንሻ፣ ሌላኛው ይህ የማያሳስበው ከሆነ ግንኙነቱ ዘላቂነት የሌለው ቢዘልቅም አንዱን አካል አልያም ሁለቱንም የሚጎዳ መሆኑ አይቀርም። ስለሆነምወደ ትዳር ከመግባት በፊት ከሃይማኖት ባሻገር መንፈሳዊ ሕይወታችን ተቀራራቢ ደረጃ ላይ መሆኑን እና እርስ በርስ መደጋገፍ መቻላችንን ማወቅ ይገባል። መደጋገፍ አልን እንጂ መደገፍ ብቻ አላልንም። እለውጠዋለሁ፣ አሻሽላታለሁ ተብሎ ወደ ጾታዊ ግንኙነት መግባት ትዕቢትንም ጭምር የሚያሳይ ነው።

መተው የምንፈልገውን ኃጢአት ለመተው፣ መልመድ የምንፈልገውን በጎ ምግባር ለመልመድ ራሳችንን ማሻሻል እና መለወጥ ያልቻልን ሰዎች ሌላ ሰው እለውጣለሁ ብሎ ማሰብ ከትዕቢት ውጭ ምን ሊሆን ይችላል? ስለዚህ ከእኛ ጋር ተቀራራቢ፣ ከተቻለም የተሻለ መንፈሳዊ ሕይወት ያለውን ሰው መምረጥ ያስፈልጋል። ብዙዎች ሰዎችን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በማግኘታቸው ብቻ መንፈሳዊ ሰዎች እንደሆኑ አስበው ሳይጠነቀቁ ወደዚህ ሕይወት ይገባሉ ከዚያም ነገሮች እንዳሰቡት ባልሆኑላቸው ጊዜ ቤተክርስቲያን ውስጥ ያሉት ሰዎች ሁሉ እንደዚያ እንደሆኑ በማሰብ መንፈሳዊ ሕይወትን እና ቤተ ክርስቲያንን ይሸሻሉ። ሐኪም ቤት ውስጥ የተገኘ ታማሚ ሁሉ ተሽሎት እንደማይወጣ እንዲሁም ቤተክርስቲያን ወስጥ ያገኘናቸው ሰዎች ሁሉ ከድካማቸው የተፈወሱ አይደሉምና መጠንቀቅ ያስፈልጋል።

ይቆየን

ወጣትነት እና እጮኝነት

በዲ/ን ኢያሱ መስፍን

ክፍል አንድ

ይህ ርእሰ ጉዳይ በጥንታውያን እንዲሁም በዘመናችን ባሉ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን ብዙ የተባለለት እና በጥልቀት ማብራሪያ የተሰጠበት ነው። በዚህ አጭር ጽሑፍ ጠለቅ ያሉትን ትምህርቶች አቆይተን ግቢ ጉባኤያት ከዚህ ጉዳይ ጋር በተገናኘ በብዛት የሚፈተኑባቸውን ለመዳሰስ እንሞክራለን።

የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የሚገኙበት ዕድሜ ትኩስ የወጣትነት ዘመን እንደ መሆኑ ተፈልጎም ይሁን ሳይፈለግ ዕድሜን ተከትሎ የሚመጣ ሁሉም ሰው የግድ የሚያልፍበትን አንድ ጥያቄ ያስተናግዳሉ። ይህም ለክርስቲያኖች ከተፈቀዱልን ከሁለቱ የሕይወት መንገዶች የእኔ ምርጫ የትኛው ነው? የሚል ነው። እነዚህ ሁለቱ መንገዶች የድንግልና ሕይወት እና የጋብቻ ሕይወት መሆናቸው ለአንድ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት አዲስ መረጃ ላይሆን ይችላል። (1ቆሮ 7፤1-2) ጌታችን እንዳለ እስከ ሕይወት ፍጻሜ ሳያገቡ ድንግልናን ጠብቆ መኖር ተከትሎት የሚመጣውን ፈተና መቋቋም የሚችሉበት ጸጋ ለተሰጣቸው ሰዎች ብቻ የሚሆን ተጋድሎ ነው (ማቴ 19፤11)። በዚህ የተጋድሎ ሕይወት ያጌጠ ቅዱስ ጳውሎስም ስለ ጋብቻ እና የድንግልና ሕይወት በስፋት ባስተማረበት መልእክቱ ክፍል ደጋግሞ እንደተናገረው ሰው ሁሉ በዚህ የተጋድሎ ሕይወት ቢኖር መልካም እንደሆነ ጠቅሶ ይህንን መቋቋም የማይችሉ ግን ቢጋቡ የሚያስመሰግን እንጂ ነውር የሌለበት መሆኑን አስተምሯል። (፩ቆሮ. ፯፥፩) እኛ ባለንበት በዚህ ዘመን ወደ ጋብቻ ለመሄድ የወሰነ ሰው ቀድሞ የሚያልፍበት የእጮኝነት ጊዜ የሚባል እጅግ ወሳኝ ደረጃ አለ።

እጮኝነት ጊዜ

የእጮኝነት ጊዜ በቅርቡ ለመጋባት ዝግጁ የሆኑ አንድ ወንድ እና አንዲት ሴት ወደ ትዳር ሕይወት ከመግባታቸው በፊት አንዳቸው ለሌላኛው የሚመቹ አጋር መሆናቸውን እና ቢጋቡ በጋራ የትዳርን ዓላማዎች ያሳካ ትዳር ሊኖራቸው መቻሉን የሚያጠኑበት ጊዜ ነው። ይህ ጊዜ አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ላደረጉ እና ዓላማውን ለተረዱ እጅግ ጠቃሚ የመሆኑን ያህል፥ ፈተና የበዛበት እና ላልተጠነቀቁ ሰዎች ደግሞ መሰናከያ ወጥመድ ሊሆን የሚችል ነው። ቤተ ክርስቲያን ‘የእጮኝነት ጊዜ’ ብላ የምትጠራው ሁለቱ ሰዎች የፍቅር ግንኙነት ከጀመሩበት አንሥቶ እስኪጋቡ ያለውን የመጠናናት ጊዜ ሲሆን ከጋብቻ እና ከእጮኝነት ውጪ የሆነ ቤተ ክርስቲያን ዕውቅና የሰጠችው ሌላ የጾታዊ ግንኙነት ሂደት የለም።

እጮኝነት መቼ?

አንድ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት ወደ ጋብቻ የሚመራውን የእጮኝነት ሕይወት መች መጀመር አለበት የሚለውን መረዳት ወደ ሕይወታችን ሊመጡ የሚችሉ ብዙ ፈተናዎችን ለማስቀረት አልያም ለመሻገር እጅግ ጠቃሚ ነው። የእድሜ እና የአካል ጉልምስና ብቻውን ወደዚህ ሕይወት ለመግባት በቂ አይደለም። የእጮኝነት እንዲሁም የጋብቻ ሕይወት ከእድሜ ባሻገር መንፈሳዊ፣ አእምሮአዊ እና ኢኮኖሚያዊ ዝግጅትን የሚጠይቅ ነው።

ሀ. መንፈሳዊ ዝግጅት

መንፈሳዊ ዝግጁነት ማለት አንድ ወጣት ሕይወቱን ከሌላ ሰው ጋር ከመጋራቱ በፊት ከአምላኩ ጋር የሚሆንበት ጊዜ ያስፈልገዋል ማለት ነው። ከእግዚአብሔር ጋር መሆን ማለት እያንዳንዱ ክርስቲያን ከአምላኩ ጋር ያለውን ጥብቅ ትስስር የሚመለከት ነው። ከእጮኝነት በፊት ያለው የወጣትነት የብቸኝነት ጊዜ በመንፈሳዊ ሕይወት ለማደግ ለሚደረግ ተጋድሎ እጅግ የተመቸ ነው። መምህራችን ቅዱስ ጳውሎስ “ያላገባ ጌታውን እንዴት ደስ እንደሚያሰኝ የጌታን ነገር ያስባል፣ ያገባ ግን ሚስቱን እንዴት ደስ እንደሚያሰኝ የሚስቱን ነገር ያስባል፤ ልቡም ተከፍሏል” (1ቆሮ 7፡32-33) እንዳለ በትዳር ሐሳብ ሳንያዝ እግዚአብሔር አምላካችንን ደስ የምናሰኝበትን ምግባር ገንዘብ ለማድረግ መታገል ያስፈልጋል። ጾም፣ ጸሎት እና ስግደትን ማዘውተር እንዲሁም ሕይወትን ንስሓ እና የቅዱስ ቁርባን ሕይወትን መምራት ለብቻችን በሆንበት ጊዜ ሊደረጉ የሚገባቸው ናቸው። እንደዚህ ዓይነት መንፈሳዊ ልምምዶች ከትዳር በኋላ የምንሞክራቸው ሳይሆን የትዳር ኃላፊነቶችን ከመቀበላችን በፊት ገንዘብ ልናደርጋቸው የሚገቡ ናቸው። ለዚህም ነው ፈረንጆቹ ‘your relationship is as good as your singleness’ የሚሉት። በብቸኝነት ጊዜ ያልነበሩንን ምግባራት ከሌላ ሰው ጋር ከሆንን በኋላ መላመድ አስቸጋሪ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።

በተጨማሪም ልቡናችን ሳይከፈል ከእግዚአብሔር በተቀበልነው ጸጋማ ዓቅማችን የፈቀደውን ያህል በእግዚአብሔር ቤት አገልግሎት በመጠመድ ከዕድሜአችን አሠራት መክፈል ያስፈልጋል። ከትዳር በኋላ አገልግሎት የሚቋረጥ ባይሆንም እንኳ እንደ ልብ ለማገልገል የሚመቸው የብቸኝነት ጊዜ መሆኑ የሚያጠራጥር አይደለም።

ሐሳቡን ስንጠቀልለው የእጮኝነት ጊዜ ይዞት የሚመጣውን ኃላፊነት ከመቀበላችን በፊት መንፈሳዊ ምግባራትን በመለማመድ በመንፈሳዊ ሕይወታችን በኩል ራስን ዝግጁ ማድረግ ያስፈልጋል። ሁሉም ኦርቶዶክሳዊ ወጣት ይህ መንፈሳዊ ዝግጁነት ሳይኖረው ወደ እጮኝነት ሕይወት ባለመግባት ራሱን ከፈተና ሊጠብቅ ይገባዋል።

ለ. አእምሮአዊ ዝግጅት

አእምሮአዊ ዝግጁነት ወጣቶች ወደ እጮኝነት ሕይወት ከመግባታቸው በፊት ከራሳቸው ጋር የሚያደርጉት ውይይት ነው። ከራስ ጋር መሆን ማለትም ራስን ማወቅ፣ ፍላጎትን መለየት፣ ደካማ ጎኖችን ማሻሻል፣ ጥንካሬን ማስቀጠል እና በአጠቃላይ “ሰው ሆኖ” ለመገኘት መሥራት ማለት ነው። ይህ ከራስ ጋር የሚደረግ ውይይት ከትዳር እና ከድንግልና ሕይወት የትኛውን እንደምንፈልግ፣ ለምን ያንን ሕይወት እንደ መረጥን አጥርቶ ከመለየት ይጀምራል። በመቀጠልም ለመረጥነው ሕይወት የተገባን እንድንሆን ራስን ማዘጋጀት ይገባል። ሁሉም ሰው የሚፈልገው የትዳር አጋር ‘ጥሩ ሰው’ ተብሎ ሊገለጽ የሚችል መሆኑ እሙን ነው። ጥሩ ሰዎችን የምንፈልገውን ያህል እኛም ለአጋሮቻችን ጥሩ ሰዎች ሆነን ልንገኝ እንደሚገባን ማሰብ ያስፈልጋል። የመጽሐፉም ትእዛዝ ‘ባልንጀራህን እንደ ራስህ ወደድ’ (ዘሌ ፲፱፥፲፰) እንደመሆኑ ሰው ራሱን ሳይወድ ባልንጀራውን ሊወድድ አይችልም። ስለሆነም የራሳችንን ሰብእና ዐውቀን እና ተረድተን፣ ደካማ አርመን እና አሻሽለን መገኘት ይኖርብናል። ያን ጊዜ ጥሩ ሰው እንዲሰጠን እግዚአብሔርን ለመጠየቅም የሞራል ብቃቱ ይኖረናል።

ብዙዎች በሚጀምሯቸው ጾታዊ ግንኙነቶች መጽናት ሳይችሉ የሚቀሩት እና ከብዙ ሰዎች ጋር በእንደዚህ ያሉ ግንኙነቶች ውስጥ እየገቡ የሚወጡት ከአጋሮቻቸው የሚፈልጉትን ነገር አስቀድመው ባለማወቃቸው ነው። ፍላጎትን መለየት መቻል ከምን ዓይነት ሰው ጋር መሆን እንደምንፈልግ እና እንደምንችል ለማወቅ እና ለመወሰን ይረዳል። ፍላጎቱን ሳይለይ ወደዚህ ሕይወት የሚገባ ሰው ግን የማያስደስቱትን እና ሊቋቋማቸው የማይችላቸውን ጠባያት እና ድርጊቶች በአጋሩ ላይ ሲያገኝ ለመለያየት ይገደዳል። የሰዎችን ጠባይ ከውጭ አይተን በአንዴ ማወቅ ባይቻልም እኛ የምንፈልገው ጠባይ ያለቸው ሰዎችን በመጠኑ መረዳት ግን ይቻላል፡፡  ስለሆነም መለያየትን ለመቀነስና ተያይዞ የሚመጣውን ጉዳት ለማስቀረት ወደ እጮኝነት ከመግባት አስቀድሞ ከራስ መክሮ፣ ስሜትን አድምጦ የራስን ፍላጎት መለየት ይገባል።

ሐ. ኢኮኖሚያዊ ዝግጁነት

ይህ በዋናነት ከገንዘብ እና ራስን እንዲሁም ቤተሰብን ለማስተዳደር ካለን ዓቅም ጋር የሚገናኝ ዝግጅት ነው። አንድ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት ወደ እጮኝነት ሲገባ በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ትዳር ለመግባት ዝግጁ መሆኑን እና የሚመሠርተውን ቤተሰብ ለማስተዳደር ዓቅም ያለው መሆኑን አስቀድሞ ማረጋገጥ ይኖርበታል። ይህም ሌሎች ዝግጅቶች ሁሉ ወደ እጮኝነት እና ትዳር ኃላፊነት ከመገባቱ በፊት አስቀድሞ የሚታሰብበት እንጂ ከገቡበት በኋላ የሚነሣ ጉዳይ አለመሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ በኢኮኖሚ ዝግጁ መሆን ማለት ከትዳር በፊት ባለጸጋ መሆን አልያም ቤት እና መኪና መግዛት የሚል ዝርዝር መሥፈርትን ማስቀመጥ ማለት ሳይሆን ራስን እና ቤተሰብን ማስተዳደር መቻላችንን እርግጠኞች መሆን ማለት ነው። ይህም ብዙዎች እንደሚያስቡት ወንዶችን ብቻ የሚመለከት ሳይሆን እኅቶችም ሊያስቡበት የሚገባ ጉዳይ ነው።

ከእነዚህ እንጠበቅ!

የእጮኝነት ሕይወት ከላይ ያነሣናቸውን እና የመሳሰሉትን መንገዶች ተጠቅሞ ዝግጁነትን ካረጋገጡ በኋላ ብቻ ሊገባበት የሚገባ ሕይወት ነው። ከዚህ ባለፈ ብዙዎች ወደዚህ ከሚገቡባቸው የተሳሳቱ ምክንያቶች ራስን መጠበቅ ያስፈልጋል። እነዚህም ሁሉም ጓደኞቼ የፍቅር አጋር አላቸው፣ እድሜዬ ገፍቷል፣ ብቸኝነት ይሰማኛል  እና የመሳሰሉት ምክንያቶች ሊሆኑ ይችላሉ።

በአንድ ዓይነት ዕድሜ ወይም አካባቢ ያሉ ሰዎች ሁሉ አንድ ዓይነት ዝግጁነት አላቸው ማለት ስላልሆነ እና ሁሉም ወደዚህ ሕይወት የገቡ ሰዎች አስበውበት እና ተገቢውን ዝግጅት አድርገው ስለማይገቡ የሌሎች ይህንን ሕይወት መጀመር እኛም እንድንገባበት በቂ ምክንያት ነው ማለት አይደለም። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “አትሳቱ! ክፉ ባልንጀራ መልካሙን አመል ያበላሻል” (፩ቆሮ ፲፭፥፴፫) እንዳለ ተገቢውን ዝግጅት ሳናደርግ ከጓደኞቻችን ያነስን እና የተበለጥን መስሎን አልያም በእነርሱ ግፊት ወደ እንደዚህ ዓይነት ግንኙነት እንዳንገባ መጠንቀቅ ያስፈልጋል።

እንኳን ሳንዘጋጅ ዝግጁ በሆንበት ጊዜ ላይ እንኳ ተገቢው ሰው ወደ ሕይወታችን ካልመጣ በትዕግሥት እና በእምነት ሆኖ የእግዚአብሔርን ፈቃድ መጠበቅ ይገባል እንጂ ዕድሜን ምክንያት አድርጎ ወደ እጮኝነት አልያም ወደ ትዳር ሕይወት መግባት አይገባም። “ለእናንተ የማስባትን አሳብ እኔ ዐውቃለሁ” (ኤር.፳፱፥፲፩) እንዳለ እግዚአብሔር በጎውን ነገር እንዲያደርግልን ምልጃ እና ጸሎታችንን ከምስጋና ጋር ለእርሱ ማሳወቅ እንጂ በአንዳች መጨነቅ አይገባንም። (ፊል. ፬፥፮)።

ዕድሜአችንን ተከትለው በሚመጡ የሆርሞን ለውጦች እንዲሁም ባለን ማኅበራዊ መስተጋብር ምክንያት በየጊዜው የሚሰሙን እንደ ብቸኝነት፣ ያለመወደድ እና ያለመፈለግ ስሜት፣ ፍትወት እና የመሳሰሉት ወደ እጮኝነት እና ትዳር እንዳይገፋፉን ትልቅ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል። እጮኛ መያዝ ለጊዜው ችግሮቹን የፈታ መስሎ ቢሰማንም የችግሩ ምንጭ ከእግዚአብሔር እና ከራስ ጋር አለመሆን እንጂ እጮኛ ማጣት አይደለምና ጊዜውን ጠብቆ ማገርሸቱ አይቀርም። በዚህ ጊዜ ራሳችንን ብቻ ሳይሆን አብሮን የሆነውን ያንን ሰውም እንጎዳለን። ክርስቲያን አዘውትሮ በሚቀበለው ቅዱስ ቁርባን ምክንያት እግዚአብሔር ሁሌም አብሮት አለ። ዕለት ዕለት በሚሳተፍበት የማኅበር ጸሎት (ቅዳሴ) አማካኝነት ከቅዱሳኑ ጋር ኅብረት አለውና አንዳች ጓደኛ ባይኖረው እንኳ መቼም ብቸኛ አይሆንም። የራበው ሰው ምግብ እንደማይመርጥ ሁሉ አንዳች ጉድለት በተሰማው ጊዜ የፍቅር ጓደኛ የሚመርጥ ሰውም ተገቢውን ጥንቃቄ ሊያደርግ አይቻለውም። ጎዶሎአችንን ለመሙላት ብቻ ብለን ወደ እጮኝነት መግባት እጅግ የከፋ ስሕተት ነው።

ፍትወትን ለማስታገስ፣ ሌሎች ሲያወሩ የሰማናቸውን፣ በየፊልሙ ያየናቸውን፣ በመጻሕፍት ያነበብናቸውን ድርጊቶች ለመሞከር እና ለማወቅ ወደ እጮኝነት መግባት በእግዚአብሔር ዘንድ የሚያስንቀን፣ ከመንግሥቱም የሚያርቀን ከመሆኑም በላይ እኛንም ሆነ ለዚህ ርኩሰት ተባባሪ ያደረግናቸውን ወዳጆቻችንን ለልብ ስብራት ለሚዳርግ መጠላላት ያጋልጣልና ለእንደዚህ ዓይነት የኃጢአት ግቦች ወደ እጮኝነት መግባት ነውር ነው።

ይቆየን፡፡

መንፈሳዊ ኅብረት

ዲ/ን ግርማ ተከተለው

መንፈሳዊ ኅብረት (የክርስቲያኖች የኅብረት ኑሮ) በክርስቶስ ያመኑ ምእመናን የሚኖራቸው አንድነት ማለት ነው። ይህ አንድነት በክርስቶስ ያመኑ ክርስቲያኖች በዕለት፣ ዕለት  እንቅስቃሴያቸው ሁሉ አብሮ በመሆን መንፈሳዊም ሆነ ሥጋዊ ሕይወታቸውን የሚያሳድጉበት፣ ለጽድቅ የሚያበቃቸውን በጎ ተግባራት የሚያከናውኑበት የኑሮአቸው አካል ነው።

በብሉይ ኪዳን ወንድም/ባልንጀራ በሥጋ ከአንድ አባት እና እናት የተወለደ፣ በጉርብትና የሚኖር እስራኤላዊን የሚያመለከት ሲሆን  እግዚአብሔር በሙሴ በኩል በሰጠው ፲ቱ ትእዛዛት ውስጥ “ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ” ሲል በጎረቤታሞች መካከል ንጹሕ ፍቅር እንዲኖር የተሰጠ ትእዛዝ ነው፡፡ (ዘሌ ፲፱፥፲፰)  በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ሰፊ ትርጉም ይዞ እናገኘዋለን፡፡ ይህም ወንድም/ባልንጀራ በክርስቶስ አንድ አካል የሆኑትን የሚያጠቃልል ነው። ለዚህም ነው መንፈሳዊ/ክርስቲያናዊ ኅብረት ማለት በክርስቶስ ያመኑ ምእመናን የሚኖራቸው አንድነት ነው የተባለው።

የክርስቲያኖች የመንፈሳዊ ኅብረት ኑሮ የተጀመረውና ጎልቶ የተንጸባረቀው በአባቶቻችን ሐዋርያት ዘመን ነው። ይህ ዘመን ፲፪ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት፣ ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት፣   ፸፪ቱ ቅዱሳን አርድእት፣ እንዲሁም በእነርሱ ትምህርት ተስበው በክርስቶስ ያመኑ ምእመናን ሁሉ በአንድነት ይኖሩበት የነበረ ዘመን ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ይህንን ሁኔታ ሲገልጽ “ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ፣ አንዲትም ነፍስ ነበሩአቸው” እንዲል፡፡ (ሐዋ. ፬፥፴፪)

በዚያ ዘመን የነበረው ኅብረት በነፍስም በሥጋም አንድ እስከ መሆን የደረሰና ሁሉም ያለውን ሀብት አንድ ላይ ከማድረጉ የተነሣ ችግራቸውን በጋራ ይወጡ የነበረበት ዘመን ነው፡፡ የመንፈሳዊ ኅብረት ኑሮ ዋና ጥቅሙም ይህ ነው፤ በሥጋም በነፍስም መረዳዳት ስለሚንጸባረቅበት።

ከዘመነ ሐዋርያት በኋላ የነበረው ኅብረት (ክርስትና) እየተስፋፋ በመምጣቱ በክርስቲያኖች ላይ የተለያዩ ፈተናዎች ይደርሱባቸው ነበር፡፡ እንደ ዘመነ ሐዋርያት ባይሆንም በመከራ ውስጥ ሆነውም መንፈሳዊ የአብሮነት ሕይወቱን አስቀጥለዋል፡፡ ይህም በየሀገራቱ አንድ ዓይነት መልክ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ ገጽታዎች የሚከናወን ሲሆን በሀገራችንም በተለያዩ መንገዶች ሲሠራበት ቆይቷል።

ቀደምት አባቶቻችን ያንን ኅብረት በሰንበቴና በጽዋ ማኅበራት ለማስቀጠል ችለዋል። መጽሐፍ ቅዱስ “ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ እነሆ፥ መልካም ነው፥ እነሆም፥ ያማረ ነው።” (መዝ. ፩፻፴፫፥፩) በማለት እንደገለጸው፡፡ አሁን ባለንበት ዘመን ደግሞ እነዚህ እየተረሱና እየተተዉ በመምጣታቸው በኅብረት ከመሆን ይልቅ በተለያዩ ምክንያቶች ግላዊ ሕይወት ላይ ትኩረት ማድረግ እየተለመደ መጥቷል።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውያን ክርስቲያኖች ሲጽፍላቸው “ሌሎች ልማድ አድርገው እንደ ያዙት ማኅበራችንን አንተው፤ እርስ በርሳችን እንመካከር እንጂ፤ ይልቁንም ቀኑ ሲቀርብ አብልጣችሁ ይህን አድርጉ” ባለው መሠረት በኅብረት ለመኖርና ቀጣይነት ላለው ሕይወት ትኩረት ልንሰጠው ይገባል። (ዕብ. ፲፥፳፭)

በዚህ ዘመን አንድነታችንን መጠበቅ ከመንፈሳዊ ፋይዳው በተጨማሪ ለህልውናችንም በጣም አስፈላጊ ስለሆነ ከበፊቱ ይልቅ አጥብቀን ልንይዘው ይገባል።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

 

ጽዮን ማርያም

“እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፥ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፥ ይህች ለዘለዓለም ማረፊያዬ ናት መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ።” (መዝ. ፻፴፩፥፲፫-፲፬) እንዲል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በመዝሙሩ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማናዊት የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነችውን የእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ዓመታዊ በዓል ኅዳር ፳፩ ቀን በድምቀት ታከብራለች፡፡

“ጽዮን” ማለት “አምባ፣ መጠጊያ” ማለት ነው፡፡ “ሰው እናታችን ጽዮን ይላል፤ በውስጥዋም ሰው ተወለደ” (መዝ. ፹፮፥፭) በማለት መዝሙረኛው ዳዊት እንደተናገረ አዳምና ልጆቹ በበደል ምክንያት ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ከተፈረደባቸው የሲኦል እሥራት ነጻ ይወጡ ዘንድ እግዚአብሔር ወልድ ከዳዊት ዘር በተገኘችው ቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን አደረ፡፡ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ማኅፀኗን ዙፋን አድርጎ ተወለደ፡፡ እኛም ኦርቶዶክሳውያን የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ አምባ መጠጊያ የሆነችውን ድንግል ማርያምን የድኅነታችን መሠረት ናትና እናከብራታለን፣ እናመሰግናታለን፣ ከፍ ከፍም እናደርጋታለን፣ በዓሏንም እናከብራለን፡፡

ታቦተ ጽዮን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትመሰላለች፡፡ ኅዳር ፳፩ ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ በዓል በተለየ መልኩ የምናከብርበት ምክንያት በርካታ ቢሆኑም በዋነኛነት ታቦተ ጽዮን በፍልስጤማውያን ተማርካ በነበረበት ወቅት ዳጎን የተባለውን ጣኦት የሰባበረችበትና ልዩ ልዩ ተአምራት የፈጸመችበትን መሠረት አድርገን ነው፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከእግዚአብሔር በታዘዘው መሠረት ሁለት ጽላት ቀርጾ፣ የእንጨት ታቦትንም ሠርቶ ወደ ተራራ ወጣ፤ “ከማይነቅዝ እንጨትም ታቦትን ሠራሁ፤ እንደ ፊተኞቹም ሁለት የድንጋይ ጽላት ቀረጽሁ፤ ወደ ተራራም ወጣሁ፤ ሁለቱም ጽላት በእጄ ነበሩ፤ እግዚአብሔርም በተራራው ላይ በእሳት መካከል የተናገራችሁን ዐሥርቱን ቃላት ቀድሞ ተጽፈው እንደነበረ በጽላቱ ላይ ጻፈ፤ እግዚአብሔርም እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ፡፡” (ዘዳ. ፲፥፩-፬) በማለት እንደተናገረው የቃል ኪዳኑን ታቦት ይዘው ወደ ምድረ ርስት ተጉዘዋል፡፡

ወደ ትርጓሜው ስንመጣ ታቦተ ጽዮን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስትሆን፣ በውስጡዋ የያዘችው የሕጉ ጽላት የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ታቦቷ ከማይነቅዝ እንጨት መሠራቷ የጌታን እናት ንጽሕናን የሚያመለክት ሲሆን በውጪም በውስጧም በጥሩ ወርቅ መለበጡዋ የቅድስናዋና ድንግል በሕሊና ወድንግል በሥጋ መሆኗን የሚያስረዳን ነው፡፡ እስራኤላውያንም በፊታቸው ታቦተ ጽዮንን ይዘው የሚገዳደሯቸውን ሁሉ ድል ይነሡ ነበር፡፡

ፍልስጤማውያን ለጦርነት በእስራኤላውያን ተነሡ፤ በአንድነትም ተሰብስበው እስራኤላውያንን ወጉአቸው፣ እስራኤላውያን ያለ ቃል ኪዳኑ ታቦት ተሰልፈዋልና በፍልስጤማውን ድል ተነሡ፡፡ የእስራኤል ሽማግሌዎችም “ዛሬ እግዚአብሔር በፍልስጤማውያን ፊት ስለ ምን ጣለን? በፊታችን እንድትሄድ ከጠላቶቻችንም እንድታድነን የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ከሴሎ እናምጣ” አሉ፡፡ ነገር ግን ቀድሞ እስራኤላውያን በድለዋልና ለፍልስጤማውያን አሳልፎ ሰጣቸው፤ ታቦተ ጽዮንም ተማረከች፡፡ (፩ኛ ሳሙ. ፬፥ ፩-፲፩) ፍልስጤማውያን እግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ወስደው ወደ ዳጎን ቤት አስገብተው ከዳጎን አጠገብ አኖሩ፡፡ በነጋም ጊዜ ዳጎን በእግዚአብሔር ፊት በግንባሩ ወድቆ አግኝተውታል፡፡

በሆነው ነገር ግር ቢሰኙም መልሰው ዳጎኑን አንስተው በስፍራው አቁመው በሩንም ዘግተው ሄዱ፡፡ በነጋም ጊዜ ግን ሲገቡ ዳጎን በግንባሩ ወድቆ ራሱ እና ሁለቱ እጆቹ ተቆርጠው ወድቀው አገኙአቸው፡፡ የእግዚአብሔርም እጅ በአዛጦን ሰዎች ላይ ከበደ፤ የአውራጃዎቿ ሰዎችም በእባጭ በሽታ ተመቱ አይጦችም በከተሞቻቸው ፈሰሱ፤ በከተማውም ላይ ታላቅ መቅሰፍት ሆነ፡፡ የቃል ኪዳኑ ታቦትም ጠንክራብናለች በማለት ከከተማቸው አውጥተው ወደ አስቀሎና ላኳት፤ የአስቀሎናም ሰዎች እጅግ ታወኩ፡፡ “እኛንና ሕዝባችንን ልታስገድሉን የእስራኤልን አምላክ ታቦት ለምን አመጣችሁብን?” ብለው ሰደዱአት፡፡ የእግዚአብሔርም ታቦት በፍልስጤማውያን ዘንድ ለሰባት ወር ቆየች፡፡ ምድራቸውም አይጦችን አወጣች፡፡ ከሕዝቡም ብዙዎች ተቀሰፉ፡፡ በመጨረሻም ከከተማቸው አውጥተው በኮረብታው ላይ ወደ አሚናዳብ ቤት ወሰዷት፤ በዚያም ለሃያ ዓመታት ቆየች፡፡

ከሃያ ዓመት በኋላም እግዚአብሔር ለዳዊት ፍልስጤማውያንን በእጁ አሳልፎ ሰጠው ድልም አደረጋቸው፡፡ “አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦት” እንዲል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የእግዚአብሔር ታቦትን ይዘው በእልልታና በዝማሬ በክብር ወደ እስራኤል ተመለሰች፡፡ ዳዊትም በተከላት ድንኳን ውስጥ አኖራት፡፡

ከዚህ ታሪክ በተጨማሪ ከላይ የኅዳር ጽዮንን በዓል የሚከበርበት ምክንያት፡-

፩. ነቢዩ ዘካርያስ ጽዮንን በተቅዋመ ማኅቶት አምሳል ያየበት፣

፪. ቀዳማዊ ምኒልክ ታቦተ ጽዮንን ይዞ አክሱም የገባበት፣

፫. በዮዲት ጉዲት ዘመን በዝዋይ ደሴት ቆይታ ሰላም ሲሆን ተመልሳ አክሱም የገባችበት፣

፬. አብርሀ እና አጽብሐ በአክሱም ከተማ ከ፫፻፴፫-፫፻፴፱ ዓ.ም ቤተ መቅደሱን ሠርተው ቅዳሴ ቤቱን ያከበሩበት ዕለት ስለሆነ ኅዳር ፳፩ ቀን ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በዓሉን በድምቀት ታከብራለች፡፡ (መድብለ ታሪክ፤ ገጽ ፻፶፪)፡፡  በታቦተ ጽዮን ከተመሰለችው ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን፡፡

“በጽዮን መለከትን ንፉ፤ ጾምንም ቀድሱ፤ ጉባኤውንም ዐውጁ” (ኢዩ.  ፪ ÷፲፭)

በኃይለ ኢየሱስ ዘጼዴንያ

ክፍል ሁለት                                                 

የጾመ ነቢያት ሰንበታት መጠሪያ

ዘመነ ስብከት

በነቢያት ጾም ውስጥ ከታኅሣሥ ፯-፲፫ ቀን ያለው ዘመን ዘመነ ስብከት ይባላል፡፡ ዘመነ ስብከት የተባለበት ምክንያትም ነቢያት የጌታን በሥጋ መምጣት አምልተውና አስፍተው በትንቢትና በትምህርት መስበካቸውን ቤተ ክርስቲያን እያሰበች ሰውን ለማዳን ወደ ምድር የመጣውን አምላክ የምትሰብክበት ወቅት በመሆኑ ነው፡፡

የዘመነ ስብከት የመጀመሪያው ሰንበት (እሑድ) ስብከት ይባላል፡፡

በዚህ ሰንበት በኦሪተ ሙሴ፣ በነቢያትና በመዝሙራት አስቀድሞ ስለ ክርስቶስ ሥጋን ተዋሕዶ ሰው መሆኑ ትንቢት ተነግሮ፣ ምሳሌ ተመስሎ፣ ሱባኤ ተቆጥሮ እንደነበር ይነገራል፤ ይሰበካልም፡፡ ስብከት ማለት ሰውን ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኝ ትምህርት ማለት ሲሆን በዚህ ሳምንት ከልደተ አብርሃም እስከ ልደተ ዳዊት ባለው ትውልድ ውስጥ ስለ ክርስቶስ ሰው መሆን የተሰበከው ስብከት ይታሰባል፡፡

በስብከት ሰንበት ወልደ እግዚአብሔር ከሙሴ ጀምሮ የተነሡ ነቢያት ስለ አምላክ ሰው መሆን የተናገሩትን ይነበባል፡፡ “ያም ቃል ሥጋ ሆነ፤ በእኛም አደረ፤ ለአባቱ አንድ እንደሆነ ልጅ ክብር ያለ ክብሩን አየን፤ ጸጋንና እውነትን የተመላ ነው፡፡” (ዮሐ. ፩÷፲፬)፤ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊትም “እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም” (መዝ ፻፵፫÷፯) በማለት ስለ ክርስቶስ ማዳን በትንቢት መነጽር ተመልክቶ የዘመረው የመዝሙር ክፍል እንዲሁ ይሰበካል፡፡

የዘመነ ስብከት ሁለተኛው ሰንበት ብርሃን ይባላል፡

ነቢያት ብርሃን ጌታ ይወለዳል ብለው ስለ መስበካቸው፣ እውነተኛ ብርሃን ይመጣል ብለው ሰለማስተማራቸው የሚታሰብበት ሲሆን በዚሁ ኢየሱስ ክርስቶስ አማናዊ ብርሃን መሆኑ ይሰበካል፤ ይዘመራልም፡፡ ከዚሁ ጋር ዘመነ ብሉይ መከራ ሥጋ፣ መከራ ነፍስ የጸናበት፣ የሰው ልጅ ብርሃን ከሆነው አምላክ ጋር የተራራቀበት ስለነበር ነቢያት ያሉበትን ያን ዘመን ጨለማ ብለው በመግለጥ የነፍሳችን ብርሃን ይወለዳል፣ እውነተኛ ብርሃን ይመጣል ብለው ስለመስበካቸው የሚታሰብበት ሳምንት ነው። በዚህ ሳምንት ከልደተ ዳዊት እስከ ፍልሰተ ባቢሎን የነበረው ፲፬ ትውልድ ይታሰብበታል፡፡

የዘመነ ስብከት ሦስተኛው ሰንበት ኖላዊ ይባላል፡፡

ኖላዊ ማለት “እረኛ” ወይም “ጠባቂ” ማለት ሲሆን በዚህ ዕለት ነቢያት የእግዚአብሔር ልጅ እውነተኛ ጠባቂ ሆኖ ይገለጣል ብለው መተንበያቸው እና ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ ጠባቂ መሆኑ ቤተ ክርስቲያናችን እያሰበች የምትዘምርበት፣ የምትቀድስበት፣ የምታመሰግንበት ዕለት ነው፡፡

ነቢያት ራሳቸውንና ሕዝበ እስራኤልን ብሎም ዓለምን እረኛቸው እንደተዋቸው በጎች በመቁጠር ስለ እውነተኛው እረኛ መምጣት ትንቢት ተናግረዋል። በዚህ ሰንበት ከፍልሰተ ባቢሎን እስከ ልደተ ክርስቶስ ድረስ ያለው አሥራ አራት ትውልድ ይታሰባል። በዚህ ዘመን እሥራኤላውያን ከሀገራቸው ተሰደው በባቢሎን ፸ ዘመን ከኖሩ በኋላ ዘሩባቤልን አንግሦላቸው ይዟቸው እንዲመለስ ተደርጓል፡፡ ከዚያ በፊት እሥራኤል ጠባቂ እንደሌለው መንጋ ተበታትነው ሲኖሩ ነቢያት ከኪሩቤል ላይ የሚገለጥ እረኛቸው እንዲገለጥ የእሥራኤል ጠባቂያቸው ሆይ፣ አድምጥ እያሉ የጠየቁበት መታሰቢያ ነው፡፡ (መዝ. ፸፱÷፩-፫)

መዝሙሩም “ኖላዊ ዘመጽአ ውስተ ዓለም ወልዱ ወቃሉ እግዚአብሔር ዘወረደ እምላዕሉ፤ የእግዚአብሔር ልጅና ቃሉ የሆነ ክርስቶስ ከላይ የወረደ ወደ ዓለም የመጣ እረኛ” የሚል ሲሆን የሚነበበው ደግሞ አንቀጸ አባግዕ የተባለው የዮሐንስ ወንጌል ክፍል ነው፡፡ (ዮሐ.፲÷፩-፳፪) እረኛ የሌለው በግ ተኩላ ነጣቂ እንዲበረታበት በበደሉ ከትጉኅ እረኛው የተለየው የሰው ልጅም በሲኦል አጋንንት በርትተውበት ሲጠቀጠቅ ኖሯል፡፡ እንዲሁም ከመንጋውና ከእረኛው የተለየ በግ እንዲቅበዘበዝ አምላኩን ዐውቆ አምልኮቱን ከመግለጽ የወጣው ሕዝብ በየተራራው መስገጃዎችን እየሠራ የሚታደገውን አምላክ በመፈለግ ሲንከራተት ኖሯል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ «እንደ በጎች ትቅበዘበዙ ነበር» እንዳለ፡፡ (፩ኛ ጴጥ፪÷፳፭) ነቢያት በዓለም ተበትነው የሚቅበዘበዙትን ሕዝቡን በቤቱ ሰብስቦ የሚጠብቃቸው እውነተኛ ቸር እረኛ እንዲወለድ ስለተናገሩ ያን ለማስታወስ ሳምንቱ ኖላዊ ተባለ፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በገና ጾም ነቢያትም ሐዋርያትም ጾመው በረከት አግኝተውበታል፡፡ እኛ ምእመናንም እንደ እነርሱ በረከትን እናገኝ ዘንድ ይህንን ጾም መጾም እንደሚገባን የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ በዚህም መሠረት የነቢያት፣ የሐዋርያት፣ የጻድቃንና የሰማዕታት አምላክ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ሐዋርያት በረከት እንዲያሳትፈን፤ መንግሥቱንም እንዲያወርሰን ሁላችንም በዚህ በጾመ ነቢያት ወቅት በጾም በጸሎት ተወስነን እግዚአብሔርን ልንማጸነው ይገባል፡፡ ለዚህም አምላከ ቅዱሳን ይርዳን አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ-: ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭፣

ቃኘው ወልዴ፣ ጾምና ምጽዋት፤ ፲፱፻፺፭ ዓ.ም፤

ተስፋዬ ምትኩ፣ ሰባቱ አጽዋማት፣ ፳፻፰ ዓ.ም

“በጽዮን መለከትን ንፉ፤ ጾምንም ቀድሱ፤ ጉባኤውንም ዐውጁ” (ኢዩ.  ፪ ÷፲፭)

ክፍል አንድ

በኃይለ ኢየሱስ ዘጼዴንያ

ጾም የሥጋን ምኞት እስከ መሻቱ ቆርጦ የሚጥል፣ ለመንፈስ ልዕልና የሚያበቃውን መሣሪያ የሚያስታጥቅ ነው፡፡ ክርስቲያን ይህን መሰል መንፈሳዊ የጦር ዕቃ እንዳይለየው አጥብቆ ይለምናል፡፡ የጦር ልምድ እንደሌለው ወታደር ጠላቱን የሚቋቋምበት የጦር ትጥቅ ሳይዝ አውላላ ሜዳ ላይ ባዶውን አይቆምም፡፡ መንፈሳዊ ውጊያን በሥጋዊ ጥበብ ማሸነፍ ስለማንችል ነው አበው አጽዋማትን በአስተምህሮአቸውና በሕይወታቸው የሰበኩልን፡፡

አጽዋማት ሲደርሱ ክርስቲያኖች የሚደሰቱት ጾም የሥጋ ፈቃድ እንዳይሰለጥንባቸው፣ ቁስለ ሥጋን በማከም፣ ቁስለ ነፍስን ስለሚፈውስላቸው ነው፡፡ ጾም የቁስል መፈወሻ ኃይለ መዊዕም (ድል ማድረጊያ) ይሆናል፡፡ ከሥጋም ከመንፈስም ተቆራኝቶ ሰውን ወደ ጥፋት የሚወስድን ክፉ መንፈስ ለማራቅም ይጠቅማል፡፡

ጾም እነዚህንና መሰል መንፈሳዊ በረከትን ስለሚያስገኝ ክርስቲያኖች ይመጣላቸው ዘንድ ይናፍቁታል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርጋ በዓመት ውስጥ የሚጾሙ አጽዋማትን ደንግጋ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ከዲያብሎስ ፈተናና ወጥመድ ያመልጡ ዘንድ አበርክታለች፡፡ እነዚህም ሰባቱ አጽዋማት በመባል ይታወቃሉ፡፡ ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)፣ ጾመ ገሀድ(ጋድ)፣ ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ሐዋርያት፣ ጾመ ድኅነት (ረቡዕ እና ዐርብ) እና ጾመ ፍልሰታ ናቸው፡፡

በዚህ ዝግጅታችን ከእነዚህ የዐዋጅ አጽዋማት መካከል አንዱ የሆነውን ጾመ ነቢያትን በተከታታይ በሁለት ክፍል እናቀርብላችኋለን፡፡

ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)  

ጾመ ነቢያት ለአዳም የተነገረው ትንቢት ማለትም፡- አዳም ስለ በደሉ በማልቀሱና ንስሓ በመግባቱ ምሕረቱ ወሰን የሌለው አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር “አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ” ተብሎ የተናገረውን የተስፋ ቃል በማሰብ ነቢያት የጾሙት ጾም ነው፡፡ በየዘመናቱ የተነሡ ነቢያት የእግዚአብሔር ወልድ መውረድ፣ መወለድ በትንቢት መነጽርነት እየተመለከቱ፣ እንዲሁም እግዚአብሔር ወደፊት ሊያደርግ ያሰበው ምሥጢር ተገልጦላቸው የራቀው ቀርቦ፣ የረቀቀው ገዝፎ እየተመለከቱ፤ ምሥጢረ ሥጋዌ እውን ሊሆን መቃረቡን በማሰብ ነቢያት ጾመውታል፡፡

ይህንንም ቅዱሳን ነቢያት የተስፋው ቃል በዘመናቸው ተፈጽሞ በዓይነ ሥጋ ለማየት ባይችሉም እግዚአብሔር “የማያደርገውን አይናገር፣ የተናገረውንም አያስቀርም” ብለው አምነው ከወዲሁ ተደሰቱ፡፡ (ኢሳ. ፶፰÷፫-፲፬)

ቅዱሳን ነቢያት ስለ እግዚአብሔር ወልድ መወለድ፣ ወደ ግብፅ መሰደድ፣ በባሕረ ዮርዳኖስ መጠመቅ፣ በትምህርተ ወንጌል ጨለማውን ዓለም ስለ ማብራቱ፣ ለሰው ልጆች ድኅነት ጸዋትወ መከራ ስለ መቀበሉና ስለ መሰቀሉ፣ ስለ ትንሣኤው፣ ስለ ዕርገቱና ስለ ዳግም ምጽአቱ ትንቢት ተናግረው አላቆሙም፤ ለአዳም የተሰጠው ተስፋ ተገልጦላቸው ለተናገሩት ትንቢትም ፍፃሜ ይደርስላቸው ዘንድ ፈጣሪያቸውን ተማጽነዋል፡፡

 ነቢያት “ይወርዳል ይወለዳል” ብለው ከጾሙ እኛ እርሱ ወርዶ፣ ተወልዶ ተሰቅሎ ካዳነን በኋላ ያለን የሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ስለምን የነቢያትን ጾም እንጾማለን? ቢሉ እንደቀደሙት ነቢያት ይወርዳል ይወለዳል እያልን ሳይሆን እነርሱ የጾሙትን ጾም በማሰብ መጾማችን ድኅነተ ሥጋ፣ ድኅነተ ነፍስ፣ በረከተ ሥጋ፣ በረከተ ነፍስ እንድናገኝበት ነው፡፡

ጾመ ነቢያት ከኅዳር ፲፭ ጀምሮ እስከ ታኅሳስ ፳፱ ቀን ድረስ ለ፵፬ ቀናት ይጾማል፡፡ በዘመነ ዮሐንስ ደግሞ እስከ ታኅሳስ ፳፰ ቀን ለ፵፫ ቀናት ይጾማል፡፡ ከእነዚህም መካከል ፵ ቀናት ጾመ ነቢያት፣ ፫ ቀናት ጾመ አብርሃም ሶርያዊ፣ እንዲሁም አርድእተ ፊልጶስ የጾሙት ጾም ሲሆን የቀረው ፩ ቀን ደግሞ የገሃድ ጾም ነው፡፡ (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ቁጥር ፭፻፷፭፣ ፭፻፷፯)፡፡

የጾመ ነቢያት ስያሜዎች

ጾመ ነቢያት በተለያዩ ስሞች ይጠራል፡፡ እነዚህም።-

ጾመ አዳም፡-  ለአዳም የተነገረው የድኅት ተስፋ ስለ ተፈጸመበት ጾመ አዳም ይባላል፡፡ አዳም በገነት ያለውን ሁሉ ይገዛ ይነዳ ዘንድ እግዚአብሔር ፈቃድ ሲሰጠው አንድ ነገር ግን ከልክሎታል፡፡ በገነት ካሉት ዛፎች ዕፀ በለስን እንዳይበላ አዘዘው፡፡ ይህንንም ተላልፎ ቢገኝ የሞት ሞትን እንደሚሞት ነገርሮታል፡፡ ነገር ግን አዳም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ጠብቆ መኖር የቻለው ለሰባት ዓመታት ከሁለት ወር ከአሥራ ሰባት ቀናት ብቻ ነው፡፡ አትብላ የተባለውንም ዕፀ በለስ በላ፤ ራቁቱንም መሆኑን ተረዳ፣ ጸጋውም ተገፈፈ፡፡ በተድላ በደስታ ከሚኖርበት ገነትም ወደ ምድረ ፋይድ ተባረረ፡፡ (ኩፋ. ፫፥፲፯-፳፬)

አዳም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መተላለፉን የሞት ሞትም እንደሚሞት በተረዳ ጊዜ ከእግዚአብሔር የተነገረውን ቃል አሰበ፤ የፀፀት ዕንባን እያነባ ይቅርታን ከአምላኩ ዘንድ ለመነ፡፡ እግዚአብሔር ቸርነቱ ወሰን የለውምና ለአዳም “አምስት ቀን ተኩል (አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን) ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ሲል ቃል ኪዳን ገባለት፡፡ (ቀሌ. ፫፥፲፯-፲፱) አዳምም ቃል ኪዳኑ ይፈጸምለት ዘንድ ጾመ ጸለየ፡፡

ይህንንም ጾም ከአዳም ጀምሮ እስከ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መወለድ ድረስ የነበሩት ነቢያት ጾመውታል፡፡ ነቢያት ለምን ጾሙት ብንል፤- ለአዳም የተገባውን ቃል ኪዳን ይፈጸም ዘንድ እየናፈቁ ከድንግል ማርያም ይወለዳል፣ በሞቱም ሞት የተፈረደበትን የሰው ልጅ ነፃ ያወጣዋል ሲሉ ነው፡፡ ለመጥቀስ ያህል ሊቀ ነቢያት ሙሴ ፵ ቀን ጾሟል (ዘፀ ፴፬÷፳፯)፤  በተጨማሪም ነቢዩ ዕዝራ፣ ሌሎችም ነቢያት ጾመውታል፡፡

ጾመ ማርያም፡- እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወልደ አብን ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ በማለት ጾማዋለችና ጾመ ማርያም ይባላል፡፡ ይህን ያለችው በመደነቅ፣ በትሕትና እና ቀደምት አባቶቿ ነቢያት ሲጾሙት አይታ ጾማዋለች፡፡ እንዴት ፀንሼ እወልደዋለሁ ማለት ጥርጥር ሳይሆን ተደምሞ፣ መደነቅ የነገረ ልደቱን አይመረመሬነት ይገልጻል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ትሕትና ነው፡፡

እግዚእሔር ወልድ በነቢያት ምሳሌ እየተመሰለ፣ ትንቢት እያናገረ አምስት ሺህ አምስት መቶው ዘመን ሲፈጸም ንጽሕት ቅድስት ከምትሆን ከእመቤታችን ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ተወልዷል፡፡ የነቢያትም ትንቢት ተፈጽሟልና የጾሙ መጨረሻ (መፍቻ) በዓለ ልደት በመኾኑም የልደት ጾም ተብሏል፡፡

ዘመነ አስተምሕሮ(አስተምህሮ)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዘመን አከፋፈል ሥርዓት መሠረት ከኅዳር ፮ ጀምሮ እስከ ታኅሣሥ ፯ ቀን ድረስ ያለው ወቅት ዘመነ አስተምህሮ ይባላል፡፡

 አስተምህሮ፡- ቃሉ በሀሌታው “ሀ” ሲጻፍ የቃለ እግዚአብሔር ማስተማሪያ (የትምህርተ ወንጌል) ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም “መሀረ – አስተማረ፤ ለመምህር ሰጠ፤ መራ፤ አሳየ፤ መከረ፤ አለመደ” ወይም “ተምህረ – ተማረ፤ ለመደ” የሚለው የግእዝ ግስ ሲሆን፣ ይኸውም የእግዚአብሔር ቸርነቱ፣ ርኅራኄው፣ ትዕግሥቱና የማዳን ሥራው በቤተ ክርስቲያን በስፋት የሚሰበክበት ጊዜ ነው፡፡

አስተምሕሮ፡- ስንል ደግሞ ቃሉ በሐመሩ “ሐ” ሲጻፍ ደግሞ የምሕረት፣ የይቅርታ ዘመን ማለት ነው፡፡ ሥርወ ቃሉም “መሐረ – ይቅር አለ፣ ዕዳ በደልን ተወ” ወይም “አምሐረ – አስማረ፤ ይቅር አሰኘ፤ አራራ፤ አሳዘነ” የሚለው የግእዝ ግስ ነው፡፡ ዘመነ አስተምሕሮ ስለ እግዚአብሔር ቸርነትና ርኅራኄ፤ እርሱ በደላችንን ሁሉ ይቅር እንደሚለን እኛ ምእመናንም እርስ በእርስ ይቅር መባባል እንደሚገባን ትምህርት የሚሰጥበት ወቅት ነው፡፡

ይህ ዘመነ አስተምሕሮ ቤተ ክርስቲያን ስለ ልጆቿ ይቅርታ የምትጠይቅበት፤ ምእመናንንም በጾም በጸሎት ተወስነው ስለ በደላቸው ይቅርታ የሚጠይቁበት፣ እግዚአብሔርንም   የሚማጸኑበት ጊዜ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ምሕረትና ይቅር ባይነትም በስፋት ትምህርት የሚሰጥበት ዘመን ነው፡፡

በዘመነ አስተምሕሮ የሚገኙ ሰንበታት፡- በቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍት እንደተቀመጠው በዘመነ አስተምሕሮ ውስጥ የሚገኙ ሰንበታት (ዕሑዶች) አስተምሕሮ፣ ቅድስት፣ ምኵራብ፣ መጻጉዕ እና ደብረ ዘይት ተብለው ይጠራሉ፡፡ ሳምንታቱን በዚህ መልክ የከፋፈለውም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ (ድጓ ዘአስተምህሮ)፡፡ ከመጀመሪያው ሳምንት (ከአስተምሕሮ) በቀር የአራቱ እሑዶቹ ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ጋር አንድ ዓይነት ነው፡፡

የዘመነ አስተምህሮ ሰንበታት (እሑዶች) ስያሜ ከዐቢይ ጾም ሰንበታት ስያሜ ጋር ተመሳሳይ ይሁን እንጂ በእነዚህ ሳምንታት ሌሊት የሚዘመሩ መዝሙራት፣ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትና የሚቀርቡ ትምህርቶች ግን በይዘትና በምሥጢር ይለያያሉ፡፡ ትምህርቶቹ በምስጢር ይለያያሉ ስንልም በዚህ ወቅት የሚነገረው ምስጢርና ይዘት በወቅቱ ላይ የሚያተኩር መሆኑን ለመግለጽ ነው፡፡

ይቆየን