በኣታ ለማርያም

ታኅሣሥ ሦስት በዚህች ቀን አምላክን የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሦስት ዓመት ሲሆናት ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ነው፡፡ እርሷ ለእግዚአብሔር የስእለት ልጅ ነበረችና፡፡

እናቷ ቅድስት ሐና ልጅ የሌላት ስለሆነች በቤተ እግዚአብሔር ውስጥ ከሴቶች ተለይታ ርቃ ትኖር ነበር፡፡ ሽማግሌ ከሆነ ከኢያቄም ከባሏ ጋርም እጅግ የምታዝን ሆነች፡፡ እግዚአብሔርም ሐዘናቸውን ሰማ፤ ቅድስት ሐናም እንዲህ ብላ ለእግዚአብሔር ተሳለች፡፡ “የሰጠኸኝን ፍሬ ለእግዚአብሔር አገልጋይ አደርገዋለሁ፡፡”

ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምንም በወለደቻት ጊዜ ሦስት ዓመት በቤቷ ውስጥ አሳደገቻት፡፡ ከዚህም በኋላ ከደናግል ትኖር ዘንድ ወደ ቤተ መቅደስ ወሰደቻት፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ስለ ምግቧ በመጨነቁ ሕዝቡን ሰብስቦ ሳለ መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፤ ዘካርያስ ለእርሱ የመጣ ሀብት መስሎት ታጥቆ እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ ከስምዖን ጀምሮ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም በተራ ቢሞክሩ በተመሳሳይ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ ብለው ሐና እና ኢያቄም እንዲቀርቡ አደረጓቸው፤ ለእነርሱም ራቀባቸው፤ ዘካርያስም ሐናን እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ ባላት ጊዜ ቅድስት ድንግል ማርያም ድክ ድክ እያለች እናቷን ስትከተል መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መግቧት ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱም ሕዝቡም የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር ብለው አስገቧት፤ ይህም ታኅሣሥ ፫ ቀን ነበር፡፡

በቤተ መቅደስም ምግቧን ከመላእክት እየተቀበለች አሥራ ሁለት ዓመት ኖረች፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ወደ ዓለም መጥቶ ከእርሷ ሥጋን እስከነሣ ድረስ፡፡

ከሴቶች ሁሉ የተመረጠች ይህቺ ናት፤ በቤተ መቅደስም በመኖር አሥራ ሁለት ዓመት ሲፈጸምላት እርሷ ለእግዚአብሔር የተሰጠች የስእለት ልጅ ናትና ለሚጠብቃት ይሰጧት ዘንድ ካህናት እርስ በእርሳቸው ተማከሩ፡፡ በሴቶች ላይ የሚደርስ በእርሷ ላይም ይደርስባታል ብለው ስለፈሩ በቤተ መቅደስ ውስጥ ይተዋት ዘንድ ለእነርሱ ትክክል መስሎ አልታያቸውም፡፡ ስለዚህም ሊጠብቃት ለሚገባው በእርሷ ላይ እጮ ለያኖሩ ወደዱ፡፡

ከዚህም አስቀድሞ ሊቀ ካህናት ዘካርያስ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን “ልጄ ማርያም ሆይ አንቺ እንዳደግሽና ለአካለ መጠን እንደደረስሽ ዕወቂ፤ ልትታጨ ትወጃለሽን? እግዚአብሔርን የሚፈራ መልካም የሆነ የተባረከ ጎልማሳ እንፈልግልሽን? ወይም በሕይወትሽ ዘመን ሁሉ በቤተ መቅደስ ተቀምጠሽ እግዚአብሔርን ልታገለግዪው የምትሺ ከሆነ በሴቶች ላይ የሚደርሰው በሚደርስብሽ ወራት ወደ ቤተ መቅደስ ደጅ ከመግባት ትጠበቂ ዘንድ በኦሪቱ የተፈጸመውን የርግማን ሥርዓት በአንቺ ላይ እንሠራለን” አላት፡፡

ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም “እነሆ እኔ የእግዚአብሔር አገልጋዩ በፊታችሁ ነኝ፤ አባትና እናት የሉኝም፤ ስሙ ቡሩክ ምስጉን ከሆነ ከእግዚአብሔር በታች ከእናትና አባት ፈንታ እናንት ናችሁና የእግዚአብሔር ትእዛዝ እንደምታውቁ አድርጉ” ብላ መለሰች፡፡

ካህናቱና ማኅበሩም ሁሉ ዘካርያስን ወደ ቤተ መቅደስ ገብተህ ስለዚህች ብላቴና ማርያም ወደ እግዚአብሔር ጸልይ አሉት፡፡ ዘካርያስም ገብቶ ሲጸልይ በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና እንዲህ አለው፡- “ዘካርያስ ሆይ ወጥተህ ከዳዊት ወገን ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን ሁሉ ወንዶች ሰብስብ፤ የእያንዳንዱንም በትር ከስሙ ጋር ውሰድ፡፡ ወደ ቤተ መቅደስም በምሽት ገብተህ ወደ እግዚአብሔር ጸልይበት፡፡ በነጋ ጊዜም በትሮቻቸውን አውጣ፡፡ እግዚአብሔርም በበትሩ ላይ ምልክት ለገለጠልህ ለዚያ ሰው ማርያምን ተቀብሎ ሊጠብቃት ይገባዋል፡፡”

ካህኑ ዘካርያስም ወጥቶ አንድነት ለተሰበሰቡት ሕዝብ የእግዚአብሔር መልአክ የነገረውን ነገራቸው፡፡ በዚያንም ጊዜ “ከዳዊት ወገን ጎልማሳም ቢሆን ሽማግሌም ቢሆን ሚስቱ የሞተችበት ሁሉ በኢየሩሳሌም ወደ አለ ቤተ መቅደስ ይሂድ” እያሉ ዐዋጅን ዙረው የሚናገሩ በእስራኤል አገር ሁሉ ላከ፡፡

ከዳዊት ወገን የሆነ ጠራቢው ዮሴፍም በሰማ ጊዜ በትሩን ይዞ ከናዝሬት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ፡፡ ካህኑ ዘካርያስም የሁሉንም በትሮች ተቀብሎ ስማቸውን በላያቸው ጻፈ፡፡ ቁጥራቸውም አንድ ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አምስት በትሮችን ወደ ቤተ መቅደስ አስገብቶ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ እንዲሁም ሰዎች ሁሉ ከቤተ መቅደስ ውጪ ቆመው ይጸልዩ ነበር፡፡ ዘካርያስም ጸሎቱን በፈጸመ ጊዜ በማግስቱ  ለእያንዳንዱ በትራቸውን አውጥቶ ሰጠ፡፡ ጠራቢው ዮሴፍም በትሩን ሊቀበል በቀረበ ጊዜ የዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩም ጫፍ ላይ ኦ ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት” የሚል ጽሑፍ አገኙ፤ ርግብም እየበረረች መጥታ በአረጋዊው ዮሴፍ ራስ ላይ አርፋለች፤ ካህናቱና ሕዝቡም ሁሉ አይተው እጅግ አደነቁ፤ ምስጉን የሆነ እግዚአብሔርምን አመሰገኑት፡፡

ዘካርያስም ዮሴፍን “ዮሴፍ ሆይ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ እንደተናገረ ድንግል ማርያምን ወደ ቤትህ ወስደህ ጠብቃት” አለው፡፡ የሴፍም ቅድስት ድንግል ማርያምን ከካህናት እጅ ተቀበላት፣ በእርሱም ዘንድ ኖረች፡፡ ከዚህም በኋላ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ስለ እግዚአብሔር ልጅ ከእርሷ ሰው ሁኖ ስለመወለዱ በዮሴፍ ቤት አበሠራት፡፡

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቃል ኪዳንና በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡ስንክሳር ታኅሣሥ ቀን

Top of Form

Bottom of Form

Top of Form

Bottom of Form

ኦርቶዶክሳዊ የአለባበስ ሥርዓት

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮዋ የሰው ሕይወትን በመልካም ጎዳና በሥጋም ሆነ በነፍስ የሚመራ ነው፡፡ ትምህርትዋም ፍጹም መንፈሳዊ ነው፡፡ የምታስተምረውም የአምላክዋን ቃል በቀጥታ ሳትቀንስ እና ሳትጨምር ሳታስረዝምና ሳታሳጥር ለሚሰማት ሁሉ ታደርሳለች፡፡ የሥርዓትዋም መነሻ እና መድረሻ ከምድር ሳይሆን ከሰማይ ነው፡፡ “ሥርዓተ ሰማይ ተሠርዐ በምድር” እንዲል፡፡ ይህም ሰማያዊውን ሥርዓት ተከትላ በምድር ያሉ አባላቶቹዋ የሰማዩን ሥርዓት በእምነት በመመልከት በምድር የሚኖሩ ሰማያውያን እንዲሆኑ የምታደርግበት ጥበብ ነው፡፡ የዚህች የሰማይ ደጅ የሆነች የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጅ ነኝ የሚል ሁሉ ሀገሩ በሰማይ እንደሆነ ላፍታም እንኳ ቢሆን ሊዘነጋው አይገባም፡፡ በዚህ ዓለም የሚኖረው እስከተፈቀደለት ዕድሜ ብቻ እንደሆነ ያስተውላልና ራሱን በምታልፍ ዓለም ውስጥ ደብቆና ደልሎ ለማይረባ አስተሳሰብ ተላልፎ አይሰጥም፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ልጆቿ ለዘለዓለም ቅዱሳን መላእክትን መስለው የሚኖሩበትን ሥርዓት በምድር ሠርታ እንዲኖሩት በማድረግ ዜግነታቸው ሰማያዊ እንደሆነ በተግባር እያሳየች ታስተምራቸዋለች፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሠራችውን ሥርዓት ሁሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ አንጻር ስንመለከተው በቀጥታ ቃሉን በተግባር ወይም በትርጉም የምንተገብርበት ነው፡፡

በዚህ ርእስም የምንመለከተው ኦርቶዶክሳዊ የአለባበስ ሥርዓት ከመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እና ከአዋልድ መጻሕፍት፣ ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ አንጻር ምን መምሰል አለበት የሚለውን በተለይም ባለንበት ዘመን ያለው የብዙ ወንዶችና ሴቶች አለባበስ ወዴት እያመራ ነው የሚለውን መነሻ በማድረግ ነው፡፡

ነገርን ከሥሩ ውኃን ከጥሩ እንዲሉ አበው አዳምና ሔዋን ከበደሉ በኋላ አካልን በቅጠል፣ በቆዳ፣ በጨርቅ መሸፈን ተጀመረ፡፡ ይህም ቅድስናቸው ንጽሕናቸው እንደ ልብስ ሆኖላቸው እንዲኖር የተሰጣቸው ሀብት ሆኖ ሳለ ሰውነታቸውን ከአስተሳሰብ ጀምሮ በተግባር በፈጸሙት በደል ምክንያት ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ስለራቃቸው ክብር ስለጎደላቸው ራቁታቸውን መሆናቸው ታወቃቸው፡፡ ስለዚህም አካላቸውን መሸፈን አስፈለጋቸው፡፡

ምክንያቱም በእግዚአብሔር ፊት ለመቆምም ሆነ በሰው ፊት ለመታየት እንደ መላእክት ንጹሕ በመሆን መንፈስ ቅዱስን ጸጋ እግዚአብሔርን መልበስ የግድ አስፈላጊ ስለነበር ነው፡፡ ከውድቀት በኋላ ግን የቀድሞው ንጽሐ ጠባይ ስላደፈብን ገነት ደግሞ ባደፈ በጎሰቆለ ማንነት የማይኖሩባት ሰማያዊት ሀገር ናትና ወደ እዚህ ዓለም ተሰደድን፡፡ በዚህ ዓለም እየኖርን ለሰማያዊት ርስት የምንበቃበትን ሥራ፣ በመሥራት የገነት ምሳሌ በሆነች በቤተ ክርስቲያን ስንኖር የአለባበስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ ሥርዓቱም በጾታ ተለይቶ እንደየ ተፈጥሮአችን የወንድ ልብስ፣ የሴት ልብስ፣ የሕፃናት ልብስ፣ የመነኮሳት ልብስ፣ የካህናት እና  የዲያቆናት ልብስ፣ የኤጲስ ቆጶሳት  የሊቃነ  ጳጳሳት  ልብስ  ተብሎ  እንደየ  መልኩና አስፈላጊነቱ የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል በጠበቀ መልኩ፣ሰማያዊውን ሥርዓት መሠረት ባደረገ መልኩ ቅድስት ቤተ ክርስቲን ሥርዓት ሠርታለች፡፡

አሁን አሁን የምንመለከተውና የምንታዘበው ግን ብዙዎቻችን ከዚህ ሥርዓት ወጣ ብለናል፡፡ ወንዱ የሴቷን፣ ሴቷም የወንዱን፣ ምእመኑ የካህኑን፣ ካህኑም የመነኮሳትን በመልበስ ሥርዓት አልበኝነት በብዙዎቻችን ላይ ይታያል፡፡

በተለይም ደግሞ በከተሞቻችን እጅግ ገዝፎ የሚታየው የሴቷ እና የወንዱ አለባበስ ቅጥ ያጣ ፍትወተ ሥጋን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ ሴት በወንድ ልብስ ስታጌጥ ከማየት የበለጠ የሥነ ምግባር ዝቅጠት የለም፡፡ አስቀድሞ እግዚአብሔር ለሙሴ የወንድም ሆነ የሴት የአለባበስ ሥርዓት መጠበቅ እንዳለበት በሕጉ መጽሐፍ አስፍሮታል፡፡

“ሴት የወንድ ልብስ አትልበስ ወንድም የሴት ልብስ አይልበስ ይህን የሚያደርግ በአምላክህ በእግዚአብሔር ዘንድ የተጠላ ነውና” (ዘዳ.  ፳፪፥፭)፡፡ ሴት የወንድን ልብስ አትልበስ ማለት በራሷ በሴቷ ስም የተሰፋ ሱሪ ትልበስ ማለት አይደለም፡፡ ያማ ከሆነ የመጥበብና የመስፋት አልያም የማነስና የማጠር እንጂ ቅርጹ ያው ሆነ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ተፈጥሮ እንደሚያስተምረን ሱሪ መልበስ ለሴት የተፈቀደ አለመሆኑን ነው፡፡ ሴት ሱሪ አለመልበስ ብቻ ሳይሆን አካሏ ተገላልጦ መታየት ስለ ሌለባት ከልብስ በመራቆትዋ ምክንያት ወንዱ በእርስዋ እንዳይሰነካከል በምኞት ኃጢአት እንዳይወድቅ አካሏን የሚሸፍን ልብስ መልበስ ስለሚገባት ነው፡፡

ተፈጥሮ አያስተምራችሁምን በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረን ሴቷ ይህንን የአለባበስ ሥርዓት ባለመጠበቅዋ ምክንያት ለሚሰናከልባት ወንድ ሁሉ ተጠያቂ ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚነግረን ኃጢአትን ያደረጋት ብቻ ሳይሆን ለኃጢአት ምክንያት የሆነው ሁሉ ከተጠያቂነት አይድንም፡፡

“በእኔ ከሚያምኑ ከእነዚህ ከታናናሾች አንዱን የሚያሰናክል የወፍጮ ድንጋይ በአንገቱ ታስሮ ወደ ጥልቅ ባሕር ቢሰጥም ይሻለዋል” (ማቴ. ፲፰፥፮)፡፡

ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይድረሰውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ከታናናሾቹ አንዱን” ያለው በምግባር ደከም ያሉትን ይባሱኑ በሚያዩት ወይም በሚሰሙት ነገር ተስበው ኃጢአትን እንዲያደርጉ ምክንያት የሚሆን ይፈረድበታል ሲል ነው፡፡

አንዳንድ እኅቶች ሌላውን የሚያሰናክል ልብስ ለምን ትለብሳላችሁ? ሲባሉ እኔን ከተመቸኝ ስለ ሌላው ምን አገባኝ የሚል መልስ መመለሳቸው ያሳዝናል፡፡ እውነት ግን ለነሱስ ቢሆን የአካልን ቅርጽ የሚያሳይ ጥብቅ ያለ ታይት መሰል ለብሶ በአደባባይ መታየቱ፣ ባታቸውን እያሳዩ አጭር ጉርድ ለብሰው ብዙዎችን ለኃጢአት መሳባቸው፣ ለወንድ የተፈቀደ ሱሪ ለብሰው የሴትነት ወጉን እርግፍ አድርገው መጣላቸው ምን ዓይነት ስሜት ይሆን የሚሰማቸው? ምቾቱስ ምን ላይ ነው? አጭር ጉርዳቸውን ጨብጠው ዝቅ ለማድረግ የሚገጥሙት ትግልና መሸማቀቅ በሚዲያዎቻችን ሳይቀር የምንታዘበው አይደል፡፡ ቁራጭ ከመሆኑም አልፎ ከስስነቱ የተነሣ የአካል ቅርጽን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ልብስ ከሰውነታቸው ጣል አድርገው ነፋስ ሲመጣ ጭራሹኑ ከላያቸው በኖ እንዳይጠፋ ጨብጦ መያዝ፣የአየሩ ሁኔታ በተቀየረ ቁጥር በብርድ መጠበሱ የቱ ላይ ነው ምቾቱ? ወይንስ ደግሞ ሌላውን በማሰናከል የሚያገኙት ደስታ፣ጥቅም አለ ማለት ነው? ከሆነ ይህ ሰይጣናዊ ሥራ ነው ለማለት ያስደፍራል፡፡

እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ቅዱሳን አባቶቻችን እንዳስተማሩን ከአለባበሳችን ጀምሮ ንግግራችን፣ አረማመዳችን፣ አኗኗራችን፣ አመጋገባችን ሁሉ በጥንቃቄ ሊሆን ይገባል፡፡ “አለባበስህ በጥንቃቄ ይሁን” እንዲል (ሃይ.አበው ዘሠለስቱ ምዕት ፳፩፥፲፪) ጥንቃቄያችንም ለእኔስ እንዲህ ዓይነት ይፈቀድልኛል? ወይስ አይፈቀድም? ለሌላውስ መሰናክል አልሆንበትም? ብሎ አስቦ በጥንቃቄ መልበስ እንዳለብን ነው አበው ቅዱሳን ያስተማሩን፡፡

አንዳንድ እኅቶችማ በዓለም ጫጫታ ውስጥ የሚለብሱት ቅጥ ያጣ አለባበስ ሳያንሳቸው በሱሪ ተወጣጥረው፣ አጫጭር ጉርዶችን ለብሰው ቤተ እግዚአብሔር ሳይቀር ለጸሎት የቆመውን ወጣት ቀልብ በመስረቅ መሰናክልነታቸው ጎልቶ የሚታይ መሆኑ ሐቅ ነው፡፡ በውኑ ቤተ ክርስቲያን የሥጋ ገበያ የሚሸመትባት፣ በምንዝር ጌጥ ራሳችንን አታለን ርካሽ የሆነውን ጠባያችን የምናንጸባርቅባት ናትን? አንድ ክርስቲያን የትም ቦታ ይሁን ምንም ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ይሁን ክርስቲያናዊ ሕይወቱን የሚያስነቅፍ የስንፍና ሥራ ሊሠራ አይገባውም፡፡ ድንገት ተሳስቶ ቢወድቅ እንኳ በንስሓ መነሣት አለበት፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንኳንስ በሕግ የተከለከለውን ሴት የወንድን ወንድም የሴትን ልብስ መልበስ ይቅርና በሕግ የተፈቀደውን መብል መብላት ወንድምን የሚያሰናክል ከሆነ አለመብላትን እንደሚመርጥ አስተምሮናል፡፡ “ነገር ግን በመብል ምክንያት ወንድሜ የሚሰናከል ከሆነ ወንድሜን እንዳላሰናክል ለዘላለም ሥጋ አልበላም (፩ኛቆሮ. ፰፥፲፫)፡፡

ይኸው ሐዋርያ “እስኪ እናንተ ራሳችሁ ፍረዱ ሴት ወደ እግዚአብሔር በምትጸልይበት ጊዜ ልትከናነብ አይገባምን? ተፈጥሮዋስ አያስረዳችሁምን? ወንድ ግን ጠጉሩን ቢያሳድግ ነውር ነው ለሴት ግን ጠጉርዋን ብታሳድግ ክብርዋ ነው ለሴት ጠጉርዋ እንደ ቀጸላ ሆኖ ተሰጥቶአታልና” (፩ኛቆሮ. ፲፩፥፲፫)፡፡

እነዚህንና በዚህ ያልጠቀስናቸውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል መሠረት በማድረግ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአለባበስ ሥርዓታችን በማያስነቅፍና ለውድቀት ምክንያት በማይሆን ይልቁንም እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ነንና በክርስቶስ ደም የከበረ አካላችንን በማያራቁት ሌላውንም በማያሰናክል መልኩ መልበስ  ክርስቲያናዊ  ግዴታችን  መሆኑን  መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ከቀደሙት እናቶቻችንና አባቶቻችን መልካም የሆነውን የአለባበስ ሥርዓት እንውረስ እነርሱ ኢትዮጵያዊነትን ከኦርቶዶክሳዊነት አንጻር አዋሕደው ሀገራዊ እሴታቸውን ጠብቀው ሃይማኖታዊም ግዴታቸውን ተወጥተው ማለፋቸው ሊያስቀናን ይገባልና፡፡

“ሁሉን መርምሩ መልካሙን ያዙ” (፩ኛተሰ. ፭፥፳፩)

ይህ መልእክት የጥናትን ምርምርን አስፈላጊነት ከምንረዳባቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ኃይለ ቃላት አንዱ ሲሆን በአካባቢያችን የምናገኛቸው በርካታ መልካም እና መልካም ያልሆኑ ነገሮችን መርምረን (ተመራምረን) ፈትነን መልካም የሆነውን ያውም የሚጠቅመንን ብቻ እንድንይዝ የተመከርንበት ኃይለ ቃል ነው፡፡

ምርምር ለእኛ በእግዚአብሔር ለምናምን ሰዎች አዲስና እንግዳ ነገር አይደለም፡፡ ቀደምት አባቶቻችን መርምረው (ተመራምረው) ችግሮቻቸውን ፈትተዋል፤ በርካታ ሥራዎችንም ሠርተዋል፡፡ ከኢአማኒነት ወደ አማኒነት የመጡ ብዙ ሲሆኑ ከእነዚህ ሰዎች መካከል አበ ብዙኃን አብርሃም ተጠቃሽ ነው፡፡ አብርሃም ፈጣሪውን ፍለጋ ተመራምሮ ከጣዖት አምላኪነት እና ሻጭነት እግዚአብሔርን ወደማመን በፍጹም ልቡ የተመለሰ ቅዱስ አባት ነው፡፡

የአባታችን የአብርሃም ምርምር ዛሬም መንገዱ ስለጠፋብን፣ ብዙ ነገር ድብቅ ሆኖብን ወዴት መሔድ፣ ምን መያዝና ወዴት ማምራት እንዳለብን ግራ ለገባን ሰዎች ምሳሌ ይሆነናል፡፡ እስቲ የአብርሃም የሕይወት ጉዞ ሒደት ምን ይመስል እንደነበር በጥቂቱ እንመልከት፡-

አብርሃም የጣዖት ጠራቢው የታራ ልጅ ሲሆን አባቱ ታራ የሠራቸውን ጣዖታት እንደ ገበያው ፍላጎት እያዋደደ ይሸጥ ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ግን አብርሃም እግዚአብሔር የሰጠውን አእምሮ ተጠቀመበት፡፡ የአባቱ ጣዖት ዐይን እያለው የማያይ፣ ጆሮ እያለው የማይሰማ፣ እግር እያለው የማይሔድ በመሆኑ “ይህ አምላክ ሊሆን አይችልም” ብሎ ዐሰበ፡፡ አባቱንም “ከዚህ ከጣዖት አምልኮ ምን ትጠቀማለህ?” ብሎ ጠየቀው፡፡ ታራም ወገኖቹ ጣዖት አምላኪ በመሆናቸው አብሮ ለመኖር እንጂ ጣዖቱ ምንም እንደማይረባው መለሰለት፡፡ (ኩፋ. ፲፥፵፪-፵፯) ከዚያም አብርሃም ወደ ገበያ ይዞት የወጣውን ጣዖት “ዐይን እያለው የማያይ፣ ጆሮ እያለው የማይሰማ፣ እግር እያለው የማይሔድን አምላክ የሚገዛ” እያለ ለገበያ ያስተዋውቅ ጀመር፡፡ ገዢዎችም “ባለቤቱ እንዲህ ያቀለለውን ጣዖት ማን ይገዛል?” እያሉ ሳይገዙት ቀሩ፡፡ ከዚያም አብርሃም ጣዖቱን በድንጋይ ቀጥቅጦና ሰባብሮ አማናዊውን አምላኩን ይፈልግ ጀመር፡፡

አብርሃም አምላኩን ለማግኘት ባደረገው ሒደት የተለያዩ ፍጥረታትን (ተራራን፣ ውኃን፣ ነፋስን፣ እሳትን፣ …) እየፈተነ አምላክ አለመሆናቸውን እያረጋገጠ ከፀሐይ ደረሰ፡፡ ፀሐይም በጨለማ ስትሸነፍ በማየቱ  አምላክ አለመሆኗን አረጋገጠ፡፡ አብርሃምም በዚህ ሁኔታ ባደረገው ምርምር መሠረት የእርሱ አምላክ በምርምር የማይደረስበት መሆኑን አረጋገጠ፡፡ ስለዚህም “አምላከ ፀሐይ ተናበበኒ፤ የፀሐይ አምላክ አነጋግረኝ” በማለት ወደ አምላኩ ተጣራ፡፡ (የኦሪት ዘፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ ምዕራፍ ፲፰) እግዚአብሔርም አብርሃምን ሰማው፤ ተገለጠለትም፡፡ በማለት በታላቅ ቃል ኪዳን ተቀበለው፡፡ “እግዚአብሔርም አብርሃምን አለው፡- ከሀገርህ፣ ከዘመዶችም፣ ከአባትህም ቤት ተለይተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ውጣ፡፡ ታላቅ ሕዝብም አደርግሃለሁ፤ እባርክሃለሁ፤ ስምህንም አከብረዋለሁ፤ ለበረከትም ሁን፡፡ የሚባርኩህንም እባርካለሁ፣ የሚረግሙህንም እረግማለሁ፣ የምድር ነገዶችም ሁሉ በአንተ ይባረካሉ” (ዘፍ.፲፪፥፩)፡፡ በመሆኑም አብርሃም ብዙ ነገሮችን ፈትኖ አምላኩን ወደ ማግኘት ደረሰ፤ እግዚአብሔርም በታላቅ በረከት ጎበኘው፡፡

ሌላው በምርምር ሒደት ከሚጠቀሱት ሰዎች መካከል ነቢዩ ሳሙኤል ነው፡፡ ነቢዩ ሳሙኤልም እግዚአብሔር አምላክ “በቀንድህ ዘይቱን ሞልተህ ሒድ፤ በልጆቹ መካከል ንጉሥ አዘጋጅቻለሁና ወደ እሴይ ወደ ቤተልሔም እልክሃለሁ” ባለው ጊዜ ለእሥራኤል ንጉሥ ይሆን ዘንድ እግዚአብሔር የመረጠውን ዳዊትን እስኪያገኝ ድረስ የእሴይን ልጆች ተራ በተራ እየጠራ ተመልክቷል፡፡ ነቢዩ ሳሙኤል በስምንተኛው ሙከራው ትክክለኛውን የእግዚአብሔርን ምርጫ አግኝቶ ቀብቶ አንግሦታል፡፡ (፩ኛሳሙ. ፲፮፥፩-፲፫) ዳዊት የእግዚአብሔር ምርጫ ሲሆን የሳሙኤል ደግሞ የጥናቱ ግኝት ሆኖ እስራኤልን ለ፵ ዓመታት መርቷል፡፡

አንዳንድ ሰዎች ጥናትና ምርምር ከቤተ ክርስቲያን ጋር ሊገናኝ አይችልም ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ የጥናትና ምርምር ቦታም ሌላ ተቋም መሆን እንዳለበት ያስባሉ፡፡ መልሱ ግን እጅግ ቀላልና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነው፡፡ “በመንገድ ላይ ቁሙ ተመልከቱም፣ የቀደመችውንም መንገድ ጠይቁ፣ መልካሚቱ መንገድ ወዴት እንደሆነች ዕወቁ፤ በእርሷም ላይ ሂዱ፤ ለነፍሳችሁ ዕረፍትን ታገኛላቸሁ” (ኤር. ፮፥፲፮) ተብሎ እንደተጻፈው ምርምር በሃይማኖት የሚቻል ብቻ ሳይሆን ሊደረግ የሚገባ መሆኑንም ጭምር የሚያሳይ ነው፡፡

ከዚህ መልእክት ሁለት ዐበይት ጉዳዮችን እንረዳለን፡፡ አንደኛው በእምነት የዛሉ ወይም መንገድ የጠፋባቸው ሰዎች ቆም ብለው እንዲያስተውሉ፣ ዝም ብለው በደመ ነፍስ ከመመራት ይልቅ በማስተዋል፣ በመራመርና በመጠየቅ ወደ ቀደመችው ወደ አማናዊቷ ቤታቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን በመምጣት ሕይወት እንዲሆንላቸው የተሰጠ ምክር እና ማስጠንቀቂያ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ የጥናትና ምርምር (Research) ዋነኛ መሣሪያዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ መነገሩ ነው፡፡

የጥናትና ምርምር ዋነኛ መሣሪያዎችን ሰንመለከት በመንገድ ላይ ቁሙ ሲል የምርምር ጥያቄ (Research questions (hypothesis)፤ ተመልከቱ ሲል (Obserevation) እና ጠይቁ የሚለው ደግሞ መጠይቅ (Questioner, intereview) ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ እነዚህም ምርምር መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት እንዳለው የምንገነዘብባቸው መልእክቶች ናቸው፡፡

ከዚህ ሌላ የምንመለከተው መመርመር ያለብን የሚታየውን ግዙፉን ዓለም ብቻ ሳይሆን ረቂቅ የሆነውን የመናፍስትን ዓለም ጭምር መሆኑን ነው፡፡ ይህም “መናፍስት ከእግዚአብሔር ሆነው እንደሆነ መርምሩ” (፩ኛዮሐ. ፬፥፩) በሚል ተገልጾ እናገኘዋለን፡፡ ከእግዚአብሔር የሆነውን መልካሙን ለመቀበል መመርመር ተገቢ መሆኑን ያሳያል፡፡

ምርምር የሚለው ቃል ዘርፈ ብዙ ነው፡ የማይዳስሰው ነገር አለ ማለት አይቻልም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “ሥራን እንዴት እንሥራ፣ እንዴትስ እናቀላጥፈው?” የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ምርምራችን ከየት ተነሥቶ የት መድረስ እንዳለበት ይነግረናል፡፡ እንዲሁም ወደ ፍጥረታት (ገብረ ጉንዳን) ሔደን በመመልከት መማር እንደምንችል የሚያሳየን ክፍል የሚያረጋግጠው ይህንኑ ነው፡፡ “አንተ ታካች ወደ ገብረ ጉንዳን ሒድ፤ መንገዱንም ተመልክተህ ቅና፡፡ ከእርሱም ይልቅ ብልህ ሁን” (ምሳ. ፮፥፮-፲፩)፡፡

ሌላው ቀርቶ የሕይወት መስመራችንን እንኳ ሳይቀር ለመወሰን በጥናት ላይ ተመሥርተን በፈቃደ እግዚአብሔር እንድንመራ ነጻ ፈቃድ ተሰጥቶናል፡፡ “እነሆ እሳትና ውኃን በፊትህ አኖርኩልህ፤ ወደፈቀድከው እጅህን ስደድ” (ዘዳ. ፴፥፲፱፤ ሲራ. ፲፮፥፲፮) አይተን መርምረን እንድንወስን፣ ግን ውኃን (ሕይወትን) ብንመርጥ እንደሚሻለን ተነግሮናል፡፡

ዓለም የምታቀርብልን ነገር ለሥጋችን የሚስማማና ጊዜያዊ ደስታን የሚፈጥርልን ስለሆነ በእርሱ ተጠቃሚ ለመሆን እንፈተናለን፤ እንጓጓለን፡፡ ሆኖም ግን የሚያጓጓ ነገር በመንፈሳዊ ሕይወታችን ላይ የሚፈጥረውን ተጽዕኖ ውጤቱን ከወዲሁ መርምረንና አገናዝበን ካላየነው ድንበሩን በማናውቀው ሁኔታ ልንጥስ ስለምንችል ሁል ጊዜ የሚገባንን ምላሽ ለመስጠት በቅድሚያ መመርመር ይገባናል፡፡

ምርምር አስፈላጊ፣ ዕውቀትን የምንገበይበትና የተሻለ ነገን ለማየት የምንጠቀምበት ነው፡፡ ይህንንም በረከት ሁል ጊዜ ለመልካም ነገር ማዋል ይገባል፡፡ “ሁሉን መርምሩ መልካም የሆነውን ያዙ” ተብለናልና፡፡ (፩ኛተሰ. ፭፥፳፩)

በአጠቃላይ የምርምር ዘርፍ ለቤተ ክርስቲያን ጠቃሚ በመሆኑ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች በቤተ ክርስቲያን ሊሠሩ የሚችሉትን ጥናትና ምርምር ዓይነቶች በመለየት የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ጉዳያችን በማለት ዐቅማቸው የፈቀደውን ያህል ምርምር በማድረግ ችግር ፈቺ የጥናት ውጤቶችን ማቅረብ ይጠበቅባቸዋል፡፡

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለጥናትና ምርምር የሚሆኑ በርካታ ጉዳዮች እንዳሉ መዘንጋት የለብንም፡፡ ለዚህም ዋናው ማሳያ በዘናችን የሚገኙ የሀገራችን የሥነ ጽሑፍ፣ የሥነ ጥበብ፣ የኪነ ሕንፃ፣ የሕግና አስተዳደር፣ የዘመን አቆጣጠር፣ የሥርዓተ ትምህርትና ማኅበራዊ ሕይወትን የመሳሰሉ ጉዳዮች በአብዛኛው በቀደሙት የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና መምህራን የተቃኙ የምርምር ውጤቶች ናቸው፡፡

ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በጥናትና ምርምር ሊደገፉ የሚገባቸው በርካታ ጉዳዮች መኖራቸውን ተገንዝቦ የጥናትና ምርምር ማእከል በማቋቋም የጥናትና ምርምር ሥራን በመሥራትና በማስተባበር ላይ ይገኛል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል ዋና ዓላማ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር በተያያዘ በማኅበራዊ፣ ምጣኔ ሀብታዊ፣ ባህላዊና የመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር እንዲካሔድ ማድረግና ቤተ ክርስቲያንም በውጤቱ ተጠቃሚ እንድትሆን ማስቻል ነው፡፡ በመሆኑም ‘ሁሉን መርምሩ መልካሙን ያዙ” በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ ጥናትና ምርምር ያደርጉ ዘንድ ሊበረታቱ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ጉባኤ ቃና፤ ፯ኛ ዓመት፣ ቁጥር ፪፤ ኅዳር ፳፻፯ ዓ.ም

ጽዮን ማርያም

“እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፥ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፥ ይህች ለዘለዓለም ማረፊያዬ ናት መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ።” (መዝ. ፻፴፩፥፲፫-፲፬) እንዲል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በመዝሙሩ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማናዊት የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆነችውን የእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ዓመታዊ በዓል ኅዳር ፳፩ ቀን በድምቀት ታከብራለች፡፡

“ጽዮን” ማለት “አምባ፣ መጠጊያ” ማለት ነው፡፡ “ሰው እናታችን ጽዮን ይላል፤ በውስጥዋም ሰው ተወለደ” (መዝ. ፹፮፥፭) በማለት መዝሙረኛው ዳዊት እንደተናገረ አዳምና ልጆቹ በበደል ምክንያት ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ከተፈረደባቸው የሲዖል እሥራት ነጻ ይወጡ ዘንድ እግዚአብሔር ወልድ ከዳዊት ዘር በተገኘችው ቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን አደረ፡፡ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ማኅፀኗን ዙፋን አድርጎ ተወለደ፡፡ እኛም ኦርቶዶክሳውያን የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ አምባ መጠጊያ የሆነችውን ድንግል ማርያምን የድኅነታችን መሠረት ናትና እናከብራታለን፣ እናመሰግናታለን፣ ከፍ ከፍም እናደርጋታለን፣ በዓሏንም እናከብራለን፡፡

ታቦተ ጽዮን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትመሰላለች፡፡ ኅዳር ፳፩ ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ በዓል በተለየ መልኩ የምናከብርበት ምክንያት በርካታ ቢሆኑም በዋነኛነት ታቦተ ጽዮን በፍልስጤማውያን ተማርካ በነበረበት ወቅት ዳጎን የተባለውን ጣኦት የሰባበረችበትና ልዩ ልዩ ተአምራት የፈጸመችበትን መሠረት አድርገን ነው፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከእግዚአብሔር በታዘዘው መሠረት ሁለት ጽላት ቀርጾ፣ የእንጨት ታቦትንም ሠርቶ ወደ ተራራ ወጣ፤ “ከማይነቅዝ እንጨትም ታቦትን ሠራሁ፤ እንደ ፊተኞቹም ሁለት የድንጋይ ጽላት ቀረጽሁ፤ ወደ ተራራም ወጣሁ፤ ሁለቱም ጽላት በእጄ ነበሩ፤ እግዚአብሔርም በተራራው ላይ በእሳት መካከል የተናገራችሁን ዐሥርቱን ቃላት ቀድሞ ተጽፈው እንደነበረ በጽላቱ ላይ ጻፈ፤ እግዚአብሔርም እነርሱን ለእኔ ሰጠኝ፡፡” (ዘዳ. ፲፥፩-፬) በማለት እንደተናገረው የቃል ኪዳኑን ታቦት ይዘው ወደ ምድረ ርስት ተጉዘዋል፡፡

ወደ ትርጓሜው ስንመጣ ታቦተ ጽዮን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስትሆን፣ በውስጡዋ የያዘችው የሕጉ ጽላት የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ታቦቷ ከማይነቅዝ እንጨት መሠራቷ የጌታን እናት ንጽሕናን የሚያመለክት ሲሆን በውጪም በውስጧም በጥሩ ወርቅ መለበጡዋ የቅድስናዋና ድንግል በሕሊና ወድንግል በሥጋ መሆኗን የሚያስረዳን ነው፡፡ እስራኤላውያንም በፊታቸው ታቦተ ጽዮንን ይዘው የሚገዳደሯቸውን ሁሉ ድል ይነሡ ነበር፡፡

ፍልስጤማውያን ለጦርነት በእስራኤላውያን ተነሡ፤ በአንድነትም ተሰብስበው እስራኤላውያንን ወጉአቸው፣ እስራኤላውያን ያለ ቃል ኪዳኑ ታቦት ተሰልፈዋልና በፍልስጤማውን ድል ተነሡ፡፡ የእስራኤል ሽማግሌዎችም “ዛሬ እግዚአብሔር በፍልስጤማውያን ፊት ስለ ምን ጣለን? በፊታችን እንድትሄድ ከጠላቶቻችንም እንድታድነን የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ከሴሎ እናምጣ” አሉ፡፡ ነገር ግን ቀድሞ እስራኤላውያን በድለዋልና ለፍልስጤማውያን አሳልፎ ሰጣቸው፤ ታቦተ ጽዮንም ተማረከች፡፡ (፩ኛ ሳሙ. ፬፥ ፩-፲፩) ፍልስጤማውያን እግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ወስደው ወደ ዳጎን ቤት አስገብተው ከዳጎን አጠገብ አኖሩ፡፡ በነጋም ጊዜ ዳጎን በእግዚአብሔር ፊት በግንባሩ ወድቆ አግኝተውታል፡፡

በሆነው ነገር ግር ቢሰኙም መልሰው ዳጎኑን አንስተው በስፍራው አቁመው በሩንም ዘግተው ሄዱ፡፡ በነጋም ጊዜ ግን ሲገቡ ዳጎን በግንባሩ ወድቆ ራሱ እና ሁለቱ እጆቹ ተቆርጠው ወድቀው አገኙአቸው፡፡ የእግዚአብሔርም እጅ በአዛጦን ሰዎች ላይ ከበደ፤ የአውራጃዎቿ ሰዎችም በእባጭ በሽታ ተመቱ አይጦችም በከተሞቻቸው ፈሰሱ፤ በከተማውም ላይ ታላቅ መቅሰፍት ሆነ፡፡ የቃል ኪዳኑ ታቦትም ጠንክራብናለች በማለት ከከተማቸው አውጥተው ወደ አስቀሎና ላኳት፤ የአስቀሎናም ሰዎች እጅግ ታወኩ፡፡ “እኛንና ሕዝባችንን ልታስገድሉን የእስራኤልን አምላክ ታቦት ለምን አመጣችሁብን?” ብለው ሰደዱአት፡፡ የእግዚአብሔርም ታቦት በፍልስጤማውያን ዘንድ ለሰባት ወር ቆየች፡፡ ምድራቸውም አይጦችን አወጣች፡፡ ከሕዝቡም ብዙዎች ተቀሰፉ፡፡ በመጨረሻም ከከተማቸው አውጥተው በኮረብታው ላይ ወደ አሚናዳብ ቤት ወሰዷት፤ በዚያም ለሃያ ዓመታት ቆየች፡፡

ከሃያ ዓመት በኋላም እግዚአብሔር ለዳዊት ፍልስጤማውያንን በእጁ አሳልፎ ሰጠው ድልም አደረጋቸው፡፡ “አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦት” እንዲል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የእግዚአብሔር ታቦትን ይዘው በእልልታና በዝማሬ በክብር ወደ እስራኤል ተመለሰች፡፡ ዳዊትም በተከላት ድንኳን ውስጥ አኖራት፡፡

ከዚህ ታሪክ በተጨማሪ የኅዳር ጽዮን በዓል የሚከበርበት ምክንያት፡-

፩. ነቢዩ ዘካርያስ ጽዮንን በተቅዋመ ማኅቶት አምሳል ያየበት፣

፪. ቀዳማዊ ምኒልክ ታቦተ ጽዮንን ይዞ አክሱም የገባበት፣

፫. በዮዲት ጉዲት ዘመን በዝዋይ ደሴት ቆይታ ሰላም ሲሆን ተመልሳ አክሱም የገባችበት፣

፬. አብርሀ እና አጽብሐ በአክሱም ከተማ ከ፫፻፴፫-፫፻፴፱ ዓ.ም ቤተ መቅደሱን ሠርተው ቅዳሴ ቤቱን ያከበሩበት ዕለት ስለሆነ ኅዳር ፳፩ ቀን ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በዓሉን በድምቀት ታከብራለች፡፡ (መድብለ ታሪክ፤ ገጽ ፻፶፪)፡፡  

በታቦተ ጽዮን ከተመሰለችው ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን፡፡

ጾመ ነቢያት

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሰባት የዐዋጅ አጽዋማትን በቀናት፣ በሳምንታትና በወራት ቀምራ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ እንጠቀምበት ዘንድ ደንግጋ አበርክታለች፡፡ ከእነዚህ አጽዋማት መካከል ደግሞ ጾመ ነቢያት አንዱ ሲሆን ኦርቶዶክሳውያን ከኅዳር ፲፭ እስከ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ዋዜማ ድረስ የምንጾመው ጾም ነው፡፡  

እግዚአብሔር ለአዳም አባታችን በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ይህንን ዓለም ያድን ዘንድ የሰውን ሥጋ ለብሶ እንደሚወለድ ነቢያት በትንቢት መነጽርነት ተመልክተው ተናግረዋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ “ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፤ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፣ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፤ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” (ኢሳ. ፯፥፥፲፬) እንዲል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ከአጥቢያ ኮከብ አስቀድሞ ከሆድ ወለድሁህ” ተብሎ እንደተጻፈው፡፡ (መዝ. ፻፱፥፫)፣ በተጨማሪም “እነሆ በኤፍራታ ሰማነው፤ ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው፤ እንግዲህስ ወደ እግዚአብሔር ማደሪያዎች እንገባለን፤ የጌታችን እግሮቹ በሚቆሙበት ቦታ እንሰግዳለን” (መዝ. ፻፴፩፥፮-፯) በማለት “ይወርዳል፣ ይወለዳል” የሚለውን የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይህን ዓለም ለማዳን በሥጋ መምጣት ተናግረዋል፡፡ ነቢያት በዚህ ብቻ ሳያበቁ ስለ ስደቱ፣ ስለ ጥምቀቱ፣ ወንጌልን ስለመስበኩ፣ መከራ ስለ መቀበሉ፣ ስለ ሞቱ፣ ስለ ትንሣኤው፣ ዕርገቱና ዳግም ምጽዓቱ በትንቢት ተናግረዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ነቢያት የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መወለድ እየናፈቁ ጾመውታልና ጾመ ነቢያት ተብሏል፡፡

የነቢያት ትንቢት ፍጻሜውን አግኝቶ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜም የአዳም ተስፋው ተፈጽሟልና “ጾመ አዳም” እየተባለም ይጠራል፡፡ የጾሙ መጨረሻም በዓለ ልደት በመሆኑ “ጾመ ልደት” ይባላል፡፡ የነቢያት ትንቢት ተፈጽሞ ጨለማውን ዓለም በወንጌል ብርሃንነት (በስብከት) አጣፍጧልና “ጾመ ስብከት” ተብሎ ይጠራል፡፡

እንደዚሁም ሐዋርያት በዓለ ልደቱን እንዴት ዝም ብለን እናከብረዋለን? ነቢያት አባቶቻችን “ይወርዳል ይወለዳል” ብለው በተስፋ እየናፈቁ ጾመውታል፤ በዓለ ትንሣኤውን ዐቢይ ጾምን ጾመን እናከብረዋለን፤ በዓለ ልደቱንም ጾመን በረከት እናገኝበታለን ሲሉ ጾመውታልና “ጾመ ሐዋርያት” ይባላል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን እንደምትፀንስ ካበሠራት በኋላ “ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?” በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ ጾማዋለችና ይህ ጾም “ጾመ ማርያም” እየተባለም ይጠራል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በነቢያት ጾም ነቢያት፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ሐዋርያት፣ ጻድቃን ሰማዕታት ጾመው በረከት አግኝተውበታልና እኛ ምእመናንም በረከትን እናገኝ ዘንድ መጾም እንደሚገባን የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ ጾመን፣ ጸልየን የበረከቱ ተሳታፊዎች ያድርገን፡፡ አሜን፡፡  

ምንጭ፡-

ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡

ጾምና ምጽዋት፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯ -፶፡፡

መንፈሳዊ ተጋድሎ

መንፈሳዊ ተጋድሎ አንድ ሰው የሚያምንበትን እምነት፣ የሚመራበትን ሕግ፣ የሚያልመውን ተስፋ እና የሚወደውን ነገር ተከትሎ ከግቡ ለመድረስ ማድረግ ያለበትን በማድረግ፣ ማድረግ የሌለበትን በመተው በነጻ ፈቃዱ ወስኖ ሙሉ ኃይሉን አስተባብሮ የሚያከናውነው የመንፈሳዊ አገልግሎት፤ ጥረትና ትግል ነው።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ ሩጫዬንም ጨርሻለሁ፤ ሃይማኖቴንም ጠብቄአለሁ፡፡ እንግዲህስ የጽድቅ አክሊል ይቆየኛል፤ ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው እግዚአብሔር በዚያ ቀን ለእኔ ያስረክባል፤ ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም፡፡” (፪ኛ ጢሞ. ፬፥፯-፰) እንዲል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ በአገልግሎቱ መጨረሻ ላይ በአገልግሎት ለተከተለው ለመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስ ይህንን ቃል ሲጽፍ በተጋድሎው ይመስለው ዘንድ፣ በኋላም ለክብር አክሊል እንዲበቃ መንገዱን ለማሳየት ነው፡፡ “የእግዚአብሔርን ቃል የነገሩአችሁን መምህሮቻችሁን ዐስቡ፤ መልካም ጠባያቸውን አይታችሁ በእምነት ምሰሉአቸው” (ዕብ. ፲፫፥፯) በማለት፡፡  

ሐዋርያው የክርስቶስን መስቀል በመሸከም፣ መከራ በመቀበል ሕይወቱን በመንፈሳዊ ተጋድሎ ፈጽሞታል። ረጅም ሐዋርያዊ ጉዞ በማድረግ በታናሿ እስያና በምድረ አውሮፓ፣ በባሕርና በየብስ በመዘዋወር የክርስቶስን የምሥራች ዜና ለብዙዎች እንዲዳረስና በጨለማም ለሚኖሩት አሕዛብ ብርሃን የሆነውን የክርስቶስን ወንጌል ሰብኳል፣ አሳምኗል፤ ብዙዎችንም ከኃጢአት ወደ ጽድቅ መንገድ መልሷል፡፡ የእርሱን ፈለግ ለሚከተሉ ሁሉም የጽድቅ ዋጋ እንደሚያገኙ አስረድቷል።

መንፈሳዊ ተጋድሎ ከፈቃደ ሥጋ ጋር የሚደረግ ውጊያ ነው። ሰው በዚህ ዓለም በተሰጠው ዘመኑ ራሱን ለፈጣሪው ለማስገዛት ከራሱ ጋር ብርቱ ተጋድሎ ማድረግ ግድ ይለዋል። ቅዱስ ጳውሎስ “ሥጋ በመንፈስ ላይ፣ መንፈስም በሥጋ ላይ ይመኛል፤ ስለዚህም እርስ በእርሳቸው ይቀዋወማሉ፡፡ ስለዚህም የምትወዱትን ልታደርጉ አትችሉም“ ብሎ የገለጸው ይህንን በሰው ሕይወት ውስጥ ያለውን የማይቋረጥ ጦርነት ነው። (ገላ. ፭፥፲፪)

ታላቁ አባት ኢዮብም “ጥንቱን በምድር ላይ የሰው ሕይወት ጥላ አይደለምን? ኑሮውስ እንደ ቀን ምንደኛ አይደለምን?” (ኢዮ. ፯፥፩) በማለት ሰው ጽኑ ጦርነት የሚያካሄድበት የጦር ሜዳ መሆኑን ገልጿል። ይህም ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ የሥጋ ፈቃዳችንን ብቻ ተከትለን እንድንጓዝ በማድረግ ከነፍስ ጋር የሚደረገው ጦርነት በተወሰነ ጊዜ ተነሥቶ የሚጠፋ ሳይሆን በሰው ዘመን ሁሉ የሚኖርና የዕድሜ ልክ ትግል ነው። ይህን የሥጋና የነፍስ ጦርነት በነፍስ አሸናፊነት ማጠናቀቅና ፈቃደ ሥጋን ድል አድርጎ ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ይገባል ።ይህም ሲባል ሥጋ ርኵስ ነው፤ ሥጋ መጥፋትና መወገድ አለበት ማለት አይደለም፤ ሥጋ በራሱ የረከሰ አይደለምና። ምክንያቱም ሥጋ የተፈጠረው በራሱ በእግዚአብሔር ነውና፡፡ አምላካችን ደግሞ ርኵስ ነገር አይፈጥርም፡፡ ሰው የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ውጤት በመሆኑም ፍጥረታትን ፈጥሮ ከጨረሰ በኋላ “እግዚአብሔርም የፈጠረውን ሁሉ እጅግ መልካም እንደሆነ አየ” እንዲል፡፡ (ዘፍ. ፩፥፴፩)

ስለዚህ ፈቃደ ሥጋን መዋጋት ማለት ተፈጥሮአዊና ንጹሕ የሆነውን ሥጋን ማጥፋት ወይም ደግሞ የሥጋን ፈቃድ ማስወገድ ማለት ሳይሆን፣ ኃጢአትን በማየት፣ በመስማት፣ በመለማመድ ያደገውን÷ ወደ ኃጢአት ያዘነበለውን ፈቃዳችንን መጐሰም /መግራት/ ማለት ነው፡፡ ይህ ፈቃድ (ኃጢአት) ሥጋን ከነፍስ ቁጥጥር ውጭ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡የሰው ሥጋዊ ባሕርዩ ምግብ ሲያጣ ይራባል፣ ይደክማል፣ ሥራ መሥራት ይሳነዋል፡፡ ሲሰጡት ደግሞ ኃጢአትን ተለማምዷልና ሌላ ፈቃድ በማምጣት ጠላት ሆኖ ይፈትነዋል፡፡ “ያዕቆብ በላ፣ ጠገበ፣ ወፈረ፣ ደነደነ፣ ሰባ፣ የፈጠረውንም እግዚአብሔርን ተወ፣ የመድኃኒቱንም አምላክ ናቀ” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ (ዘዳ. ፴፪፥፲፭)

ሰውነት የሚፈልገውን ሁሉ እንደ ልቡ ካገኘና ያለ ገደብ የሚቀለብ ከሆነ ወደ ኃጢአት ለመገስገስ የተዘጋጀ መርከብ ነው፡፡ ሰውነት በተመቸውና ፈቃዱን ለመፈጸም ኃይል ባገኘ ጊዜ ነፍስ እየደከመች ትሄዳለች፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሰውነት ፈጽሞ ከደከመና ከዛለ ሥራ መሥራት ያስቸግራል፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው “ሰውነቴን እየጎሰምሁ አስገዛዋለሁ” እንዳለ፡፡ (፩ኛ ቆሮ. ፱፥፳፯) በአግባቡ ሊያዝና ሊገራ ይገባዋል፡፡ በአጠቃላይ ቅዱስ ጳውሎስ “ወንድሞቻችን አሁንም በሥጋችን ሳለን በሥጋ ፈቃድ እንኖር ዘንድ አይገባም፡፡ እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞታላችሁ፤ ነገር ግን በመንፈሳዊ ሥራችሁ የሥጋችሁን ፈቃድ ብትገድሉ ለዘለዓለም በሕይወት ትኖራላችሁ፡፡” (ሮሜ ፰፥፲፫) እንዳለ ከፈቃደ ሥጋ ጋር በመጋደል ፈቃደ ሥጋችንን ለፈቃደ ነፍሳችን ማስገዛት ይገባናል፡፡

ስለዚህ እያንዳንዳችን በተሰጠን ጸጋ መሠረት የሐዋርያውን ትምህርትና አርአያ ተከትለን እንደ ስጦታችን እና እንደ ችሎታችን መንፈሳዊ ሩጫችንን ልንሮጥ ይገባናል፡፡ ቅዱሳን ሥጋቸውን ለነፍሳቸው በማስገዛት እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ በተጋድሎ ዲያብሎስን ድል ነሥተውታልና እነርሱን አርአያ አድርገን መከራውን ሳንሰቀቅ በትዕግሥት መንግሥተ እግዚአብሔር የሚያስገባንን መንፈሳዊ ተጋድሎ እየፈጸምን እንሩጥ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለዕብራውያን ክርስቲያኖች ሲጽፍ እንዲህ ይላል፡- “እንግዲህ እነዚህ የሚያህሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን እኛ ደግሞ ሸክምን ሁሉ የኃጢአትንም ጭንቀት ከእኛ አስወግደን ከፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፡፡” (ዕብ. ፲፪፥፩-፪) ይህ ሩጫ ወደ ክብር አክሊል ያደርሰናል፡፡    

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያወጣው መመሪያ ተቃውሞ አስነሣ

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሃይማኖታዊ ነፃነታችንን የሚጋፋ መመሪያ አውጥቷል ሲሉ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ገለጹ፡፡ ተማሪዎቹ ይህንን ያሉት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በ፳፻፲፯ዓ.ም ያወጣውን የሥነ ምግባርና ዲሲፕሊን መመሪያ ተከትሎ ነው፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ወደ መመገቢያ አዳራሽ ሲሄዱ ነጠላ እንዳይለብሱና ምግብ እንዳያወጡ ሃይማኖታዊ መብታቸውን የሚጋፋ የሥነ ምግባርና ዲሲፕሊን መመሪያ መውጣቱን አቶ አበበ በዳዳ የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ኃላፊ ለማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ገልጸዋል። አቶ አበበ በዳዳ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ኦርቶዶክሳውያን የከፍተኛ ተቋማት ተማሪዎች ሃይማኖታዊ የመብት ጥሰት እንዳይፈጸምባቸው ከሚመለከታቸው አካላት ጋር መወያየት እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡

ዩኒቨርሲቲው በ፳፻፲፯ ዓ.ም ባወጣው የሥነ ምግባር ዲስፕሊን መመሪያ “የተለያዩ እምነት ተከታይ ተማሪዎች በግቢው ስለሚያስተናገድ ከሃይማኖትና ከበዓላት ጋር የተያያዙ የአለባበስ ሥርዓቶች፣ የማንነትና የእምነት መገለጫዎች በመሆናቸው ሊከበሩ ይገባቸዋል” ይላል፡፡

በሌላ በኩል የኒቨርሲቲው ሃይማኖታዊ ነፃነታችንን የሚጋፋ መመሪያ አውጥቷል ሲሉ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም “በምግብ ሰዓት የኅሊና ጸሎት ካልሆነ በቀር ጸሎት እንዳናደርግና ከዳቦ ውጭ ምግብ እንዳናወጣ እንዲሁም በመመግቢያ አዳራሽ ውስጥ ነጠላ እንዳንለብስ መመሪያ ወጥቷል” ብለዋል፡፡

ተማሪዎች አክለውም የወጣውን መመሪያ ምክንያት በማድረግ በአንዳንድ የጥበቃ አካላትና ግለሰቦች ጫና እየተደረገብን ነው ሲሉም ጠቁመዋል፡፡ ምግባችንን አውጥተን ለነዳያን መስጠትና መንፈሳዊ ጉዞ በምናከናውንበት ወቅት አውጥተን መጠቀም እንዳንችል ተደርጓልም ብለዋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ኃላፊ አቶ አበበ በዳዳ ዩኒቨርሲቲው በመጀመሪያው ረቂቅ መመሪያ ያወጣቸው ሕጎች ለኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች በጣም አስቸጋሪ ነበሩም ብለዋል፡፡ ነገር ግን በተማሪዎች በተቋቋመ ኮሚቴ በመመሪያው አንዳንድ አንቀጾች ላይ ማሻሻያ እንዲደረግ በቀረበው አስተያየት መሠረት ከበፊቱ የተሻለ ቢሆንም አሁንም ግን የተማሪዎችን ሃይማኖታዊ መብት የሚጋፋ መመሪያ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የማስተባበሪያው ኃላፊ አክለውም በተለይም ነጠላን አላስፈላጊ ልብስ በማለት የተገለጸው መመሪያ አግባብነት የሌለው ነውም ብለዋል፡፡

በመጨረሻም ይህ አካሄድ ሀገርን የማይጠቅም በመሆኑ ሊታሰብበት እንደሚገባ አሳስበው ዩኒቨርሲቲው አሳማኝ ማስረጃ ማቅረብ የሚችሉ ሰዎች በልዩ ሁኔታ ሃይማኖቱ የሚፈቅደውን አለባበስ መልበስ ይችላሉ የሚል መመሪያ ስላለው የሚመለከታቸው አካላት ውይይትና ምክክር እንዲያደርጉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

ምንጭ፡- በማኀበረ ቅዱሳን ብሮድካስት አገልግሎት

“ልጄን ከግብፅ ጠራሁት” (ማቴ. ፪፥፲፭)

ክረምቱ ለገበሬው ከባድ የሥራ ወቅት ነው፡፡ ማጡንና ድጡን፣ ዝናቡንና ጎርፉን ታግሦ በሬዎቹን ጠምዶ ሲያርስ፣ ሲጎለጉልና ምድሪቱ ዘር ታቀበል ዘንድ ሲያዘጋጅ ይቆያል፡፡ እግዚአብሔርም መልካም ፍሬ እንደሚሰጠው በማመን ዘሩን ወዳለሰለሰው መሬት ይበትናል፤ ይንከባከባል፣ አረሙንም እየነቀለ ለፍሬ ይበቃ ዘንድ ብርሃንን እየናፈቀ በተስፋ ይቆያል፤ ክረምቱ አልፎም የመጸው ወቅት ይተካል፡፡ ተራሮች፣ ሜዳና ሸንተረሩ ሁሉ ልምላሜን ይላበሳሉ፣ አበቦች ይፈካሉ፤ ገበሬው በክረምት ሲደክምበት የከረመውን እርሻ በልምላሜ ያጌጣል፣ ፍሬ ለመያዝም ደረስኩ ደረስኩ እያለ የገበሬውን ልብ በተስፋ ይሞላል፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን በዚህ በልምላሜ ወቅት ከመስከረም ፳፮ ጀምሮ ያሉት ፵ ቀናት ዘመነ ጽጌ ተብሎ ይጠራል፡፡ ይህ ወቅት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ከአረጋዊው ዮሴፍና ሰሎሜ ጋር ወደ ግብፅ የተሰደደችበትን ጊዜ ታስባለች፡፡

በእነዚህ ሳምንታትም ዕለተ ሰንበት ከዋዜማው ጀምሮ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ካህናትና ምእመናን ከምሽቱ ሦስት ሰዓት ጀምሮ የእመቤታችንን ስደት በማስመልከት በአባ ጽጌ ድንግል የተደረሰውን “ማኅሌተ ጽጌ” ፣ የተሰኘው ድርሰቱ፣ በቅዱስ ያሬድ መዝሙር እመቤታችንና ጌታችንን ወደ ግብፅ የተሰደዱበትን ወቅት በማስመልከት ያመሰገነበትን ጸሎት እንዲሁም በዝማሬ፣ በሽብሸባ፣ በእልልታና በጭብጨባ በድምቀት ያነጋሉ፡፡ እመቤታችንን በአበባ፣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስን ደግሞ በፍሬ እየመሰሉ ሊቃውንቱ ያመሰግናሉ፡፡

አዳም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመተላለፉ ምክንያት የዲብሎስ ባሪያ ሆነ፤ ፈጣሪውን አጥቷልና ተሸሸጎ የጸጸት ዕንባን አነባ፡፡ የአዳምን መጸጸት የተመለከተው እግዚአብሔርም “ከአምስት ቀንና ግማሽ ቀን በሃላ እምርሃለሁ፤ ይቅርታም አደርግልሃለሁ፤ በይቅርታ ብዛትና በምሕረቴ ብዛት ወደ አንተ ቤት እወርዳለሁ፤ በወገንህም ከርስ አድራለሁ፤ ይህ ሁሉ ስለ አንተ ደኅንነት ሆናል፡፡” (ቀሌ. ፫፥፲፱) በማለት ቃል ኪዳን ገባለት፡፡ ጊዜው ሲደርስም አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ ባርነት ነፃ ያወጣ ዘንድ በቅዱስ ገብርኤል ብስራት ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍሷ ነፍስን ተዋሕዶ በቤተልሔም በከብቶች ግርግም ተወለደ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሲወለድ ሰብአ ሰገል ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ፡፡ እንዲህ ሲሉ፡- “ኮከቡን ከምሥራቅ አይተን እንሰግድለት ዘንድ መጥተናልና የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው?” ሲሉ ጠየቁ፡፡ በይሁዳ፣ በገሊላና በሰማርያ የሮማውያን ተወካይ የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ የጌታችን ንግሥና ምድራዊ ንግሥና መስሎት መንግሥቴን ሊቀማኝ ነው ብሎ ደነገጠ፡፡ ፊሪሳውያን መሲህ ተወልዶ ከሮማውያን አገዛዝ ነፃ ያወጣናል፡፡” ብለው ያምኑ እንደነበር ስለሚያውቅም ይህ የተፈጸመ መስሎት ጭንቀቱ በረታ፡፡ የተወለደውን ሕፃንም ለመግደል ተነሣ፡፡ (ማቴ. ፪፥፩-፫)

ሄሮድስም ሰብአ ሰገልን አስጠርቶ “ሄዳችሁ የዚህን ሕፃን ነገር ርግጡን መርምሩ፣ ያገኛችሁትም እንደሆነ እኔም መጥቼ እሰግድለት ዘንድ በእኔ በኩል ተመልሳችሁ ንገሩኝ” በማለት ተናገራቸው፡፡ (ማቴ. ፪፥፰) ሰብአ ሰገልም በኮከቡ እየተመሩ ጉዞአቸውን ቀጥለው ጌታችንን ከእናቱ ጋር አገኙት፤ ተንበርክከው ሰገዱለት፤ ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ እጅ መንሻ አቀረቡለት፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ሄሮድስ እንዳይመለሱ፤ ነገር ግን መንገድ ቀይረው ወደ ሀገራቸው እንዲሄዱ በነገራቸው መሠረት በሌላ መንገድ ወደ መጡበት ተመለሱ፡፡

እነርሱም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ “ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሥ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሸ፤ እስክነግርህም በዚያ ተቀመጥ አለው፡፡” አረጋዊው ዮሴፍም ሳይጠራጠር እመቤታችንና ጌታችንን እንዲሁም ረዳት ትሆናቸው ዘንድ ሰሎሜን አስከትሎ “ልጄን ከግብፅ ጠራሁት” ተብሎ በነቢይ የተነገረው ፈጸም ዘንድ ወደ ግብፅ ወረደ፡፡ (ማቴ. ፪፥፲፫-፲፬) ሄሮድስም ሰብአ ሰገል እንዳታለሉት በተረዳ ጊዜ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስን ያገኘ መስሎት የቤተልሔምን አንድ መቶ አርባ አራት ሺህ ሕፃናትን በግፍ አስገደለ፡፡ ቤተልሔምና አውራጃዎቿም ሄሮድስ ባስገደላቸው ሕፃናት ደም ተጥለቀለቀች፡፡

ለሦስት ዓመት ከስድስት ወር በግብፅ ብዙ ጸዋትወ መከራዎችን እየተቀበሉ ከቆዩ በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይፈልገው የነበረው ሄሮድስ ሞተ፡፡ ሄሮድስም ከሞተ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በግብፅ ለዮሴፍ በሕልም ታየው፡፡ እንዲህ ሲል፡- “የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሙተዋልና ተነሥተህ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ” አለው፡፡ ኅዳር ፮ ቀንም ግብፅ ከምትገኘው ቁስቋም የምትባል ቦታ ደረሱ፡፡ በዚያም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ቤት ተከበረ፡፡ አረጋዊው ዮሴፍም ሕፃኑንና እናቱን ይዞ ወደ እስራኤል ምድር ገባ፡፡” (ማቴ. ፪፥፲፱-፳፩)

ይህንን የእመቤታችን ከልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ግብፅ መሰደድን፣ በዚያም የደረሰባቸውን መከራ በማሰብ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በረከት ያገኙ ዘንድ በጾም፣ በስግደት እንዲሁም ልዩ ልዩ የትሩፋት ተግባራትን በመፈጸም ወቅቱን ያስቡታል፡፡ ኅዳር ፮ ቀንም የእመቤታችንን ወደ ቁስቋም መድረስ ምክንያት በማድረግ በቁስቋም ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከዋዜማው ጀምሮ በሰዓታቱ፣ በዝማሬ በማሳለፍ፣ ታቦት ወጥቶም በሥርዓተ ንግሥ ይጠናቀቃል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“በሚሞት ሰውነታችሁ ኃጢአትን አታንግሡአት” (ሮሜ. ፮፥፮)

በእንዳለ ደምስስ

ኃጢአት የሚለው ቃል “ኃጥአ” ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙም፡- አጣ፣ መገፈፍ፣ መነጠቅ ማለት ነው፡፡ አዳም አባታችን ለሰባት ዓመታት በገነት ፍጥረታትን እየገዛና እያዘዘ በተድላና ደስታ ሲኖር በምክረ ከይሲ ተታሎ አትብላ የተባለውን ዕፀ በለስ በላ፣ ኃጢአትንም በራሱ ላይ አነገሣት፣ የእግዚአብሔርንም ትእዛዝ ተላለፈ፡፡ በዚህም ምክንያት ክብሩን አጣ፣ ጸጋውም ተገፈፈ፣ በእግዚአብሔር የተሰጠውንም የገዢነት ሥልጣን ተነጠቀ፣ እስከ መረገምም አደረሰው፡፡ “ከእርሱ እንዳትበላ ከአዘዝኩህ ከዚያ ዛፍም በልተሃልና ምድር በሥራህ የተረገመች ትሁን፤ በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ፤ እሾህና አሜከላ ታበቅልብሃለች፣ የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፤ ወደ ወጣህበት ምድር እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ ትበላለህ፣ አፈር ነህና ወደ አፈርም ትመለሳለህና” ተብሎ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ፣ ገነትን ያህል ቦታ አጣ፤ወደ ምድረ ፋይድም ተባረረ፡፡ ዘለዓለማዊ ሆኖ የተፈጠረው የሰው ልጅ በራሱ ላይ ኃጢአትን አንግሧልና ዘለዓለማዊነትን አጣ፤  ይህ ፍርድ የኃጢአት ሥራ ያስከተለው ውጤት እንደሆነ እንረዳለን፡፡  

አዳም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መተላለፉን በተረዳ ጊዜ ኃፍረቱን ይሸፍን ዘንድ ቅጠልን አገለደመ፣ ተሸሽጎም በደሉ ዕረፍት ነስቶት በጸጸት አለቀሰ፡፡ (ዘፍ. ፲፯-፲፱) እግዚአብሔር ፍርዱ እውነተኛ ነውና ሞት በምድር ላይ ነገሠ፡፡ አዳምም ከነበረው ክብር ወረደ፤ “የኃጢአት ትርፍዋ (ደመወዝዋ) ሞት ነውና” (ሮሜ. ፮፥፳፫) ተብሎ እንደተጻፈ በወዙና በላቡ ይበላ ዘንድ እሾህና አሜኬላውን እየመነጠረ ምድርንም እየቆፈረ ሕይወቱን ለማቆየት ታገለ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ፍጹም ቸር ነውና የአዳምን ንስሓ ተመልክቶ “አምስት ቀን ተኩል ሲሆን ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ” (ቀሌ. ፫፥፱) ባለው አምላካዊ ቃሉ መሠረት አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ይህንን ዓለም ያድን ዘንድ ተወለደ፡፡ 

መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስም “እነሆ የዓለሙን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ፡፡ ከእኔ በፊት የነበረ ሰው ከእኔ በኋላ ይመጣል ብዬ ስለ እርሱ የነገርኋችሁ ይህ ነው፤ እርሱ ከእኔ አስቀድሞ ነበርና፡፡ ነገር ግን እስራኤል እንዲያውቁት ስለዚህ እኔ በውኃ ላጠምቅ መጣሁ፡፡” (ዮሐ. ፩፥፳፱-፴፩) ሲል የመሠከረለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገባው ቃል መሠረት በዚህ ምድር ላይ ተመላለሰ፡፡ ወንጌልን አስተማረ፣ ድውያንን ፈወሰ፣ በቀራንዮ አደባባይ በመስቀል ላይ ተሰቀለ፣ ሞተ፣ ተቀበረ፣ በትንሣኤውም ትንሣኤያችንን አወጀ፡፡ አዳምና ልጆቹንም ወደ ቀደመ ክብራቸው መለሰ፡፡

እግዚአብሔር ኃጢአትን እንጂ ኃጢአተኛን አይጠላምና የተከፈለልንን ዋጋ አስበን እንደ ቃሉም ተጉዘን፣ የተሰጠንን ክብር ጠብቀን መገኘት ከእኛ ከኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ሰዎች በላከው መልእክቱ “በሚሞት ሰውነታችሁ ኃጢአትን አታንግሡአት” (ሮሜ ፮፥፮) ሲል የሚያሳስበን፡፡

ኃጢአት ከእግዚአብሔር አንድነት ይለያል፣ ሥጋንና ነፍስን ያጎሳቁላል፣ በመጨረሻም ወደ ሞት ያደርሳል፡፡ በተለይም በርካታ ወጣቶች ይጉዳቸው ወይም ይጥቀማቸው ሳያመዛዝኑ ሁሉንም የመሞከር ችግር በከፍተኛ ደረጃ ስለሚታይባቸው በቀላሉ ኃጢአትን ለመለማመድ ይፈጥናሉ፡፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ወጣትነትን የእሳትነት ዘመን መሆኑን ታስተምራለች፡፡ ይህንን የእሳትነት ዘመንን በመንፈሳዊነት ማረቅ፣ መግራት ካልተቻለ ጥፋቱ ከራስ አልፎ ቤተሰብን፣ ማኅበረሰብንና ሀገርን እንዲሁም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ይጎዳል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስ “አንተ ግን በተማርህበትና በተረዳህበት ጸንተህ ኑር፤ ከማን እንደተማርኸው ታውቃለህና” (፪ጢሞ. ፫፥፲፬) እንዲል ከእግሩ ሥር ቁጭ ብሎ በመማሩ፣ የሚያከናውናቸውን መንፈሳዊ ተግባራት ሁሉ በማገዝና በመሳተፍ መንፈሳዊነትን ገንዘብ አድርጓልና ወጣትነቱን ተጠቅሞበታል፡፡ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብሎ ሲማርና ሲያገለግለው የነበረው ደቀ መዝሙሩ ዴማስ ግን የወጣትነት ስሜቶች ተገዢ ሆኖ ለዓለም እጁን በመስጠት፣ ብልጭልጯ የተሰሎንቄ ከተማ ማርካው ከአገልግሎቱ አሰናክላ ጥላዋለች፤ ኃጢአትንም በራሱ ላይ አነገሣት፡፡ “ዴማስ ይህንን የዛሬውን ዓለም ወድዶ እኔን ተወኝ፤ ወደ ተሰሎንቄም ሄደ” (፪ጢሞ. ፬፥፲) እንዲል ፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎቻችንም በወጣትነት ዕድሜ ላይ የሚገኙ በመሆኑ ከቤተሰብ የሚርቁበት፣ በራስ መተማመን የሚያዳብሩበት፣ ለዓለሙም ሆነ ለመንፈሳዊው ዓለም ራሳቸውን አጋልጠው የሚሰጡበት ጊዜ ላይ በመሆናቸው በማስተዋል ራሳቸውን ሊመሩ ይገባል፡፡ ሥጋዊ ፍላጎትና የጓደኛ ግፊት ሳይበግራቸው ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ የሚታገላቸውን የኃጢአት ቀንበር አሽቀንጥረው በመጣል በመንፈሳዊ ሕይወት መታነጽ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ዲያብሎስ ዙሪያቸውን አጥሮ ከመንገዳቸው ሊያስወጣቸው እንቅልፍ እንደሌለው በመረዳት ከምን ጊዜውም በላይ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደትና በአገልግሎት በመትጋት ድል ሊነሡት ይገባል፡፡ “እንግዲህ ዐዋቂዎች ሁኑ፣ ትጉም፣ ጠላታችሁ ጋኔን የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሳ አንበሳ ይዞራልና፡፡ እርሱንም በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት” በማለት ቅዱሰ ጳውሎስ እንዳስተማረው፡፡ (፩ጴጥ. ፭፥፰-፱)

በሁለቱም ወገን ማለትም ዓለማዊውን ጥበብ በመንፈሳዊ ጥበብና ዕውቀት በመግራት ሀገርንና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለመጥቀም ትክክለኛ ጊዜው የወጣትነት ጊዜ ነው፡፡ ይህን ጊዜ በዋዛ ፈዛዛ ማሳለፍ ስለማይገባ ከእግዚአብሔር የተሰጠንን የወጣትነት የዕድሜ በረከት ልንጠቀምበት ያስፈልጋል፡፡ “በሚሞት ሰውነታችሁ ኃጢአትን አታንግሡአት” (ሮሜ. ፮፥፮) ተብለን እንደተማርን መንፈሳዊነትን ለጽድቅ አገልግሎት በማዋል ዓለም ከዘረጋችውና ካጠመደችው የኃጢአት ወጥመድ ልንርቅ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር 

የጥያቄዎቻችሁ መልስ:- ከሱስ መላቀቅ አቃተኝ

ክፍል ሁለት

የሁለተኛ ዓመት የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተማሪ ነኝ፤ ተወልጄ ያደግሁት በአነስተኛ የገጠር ከተማ ነው፡፡ በመንደራችን ጫት የሚቅም ሰው አይደለም ጫት ምን እንደሆነ በተግባር አይታወቅም ማለት ይቻላል፡፡ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም በገባሁ አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በጓደኞቼ ግፊት ጫት መቃም ለንባብ ይረዳል በሚል ሰበብ የጫት ተጠቃሚ ሆንኩ፡፡ አሁን ከጫት ቃሚነት አልፌ በተለያዩ ሱሶች ተይዣለሁ፡፡ ከእነዚህ ሱሰሶች ለመላቀቅ በተለያዩ ጊዜያት ሞክሬአለሁ፤ ነገር ግን አልተሳካልኝም፡፡ ይህ የሁል ጊዜ ጭንቀቴ ነውና ምን ትመክሩኛላችሁ?

ገብሬ (ከሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ)

“ከሱስ መላቀቅ አቃተኝ” በሚል ገብሬ (ከሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ) ልኮልን በክፍል አንድ ዝግጅታችን ከተያዘባቸው ልዩ ልዩ ሱሶች በቁርጠኝነት መውጣት እንዲችል መ/ር ፍቃዱ ሳህሌ ሁለት መሠረታዊ ነጥቦችን አንስተዋል፡፡ እነዚህም፡- ምክንያቱን በሚገባ መመርመር እና የሚያስከትለውን ጉዳት ማጤን የሚሉ ንዑስ ርእሶችን አንስተው አብራርተውልናል፡፡ በክፍል ሁለት ዝግጅታችን ደግሞ ሊወሰዱ የሚገባቸው ርምጃዎች ላይ በማተኮር ያቀርቡልናል፡፡

ሀ. መወሰን

ይህ የመጀመሪያው መሠረታዊ ርምጃ ነው፡፡ አንድ ሰው ሳይወስን ምንም ነገር ማድረግ አይችልም፡፡ ከጥያቄህ እንደተዳነው ከሱሶች ለመላቀቅ ፍላጎት አለህ፤ ይህ ደግሞ ለመወሰንህ በቂ መነሻ ነው፡፡ ፍላጎትና ውሳኔ ግን ተመጋጋቢነት እንጂ አንድነት የላቸውም፡፡ ብዙ ሰዎች ፍላጎት ይኖራቸውና ውሳኔ የመወሰን ዐቅም ያጣሉ፡፡ ውሳኔ የመወሰን ዐቅም ምክንያቱንና ውጤቱን በሚገባ በማወቅ ላይ ተመሥርቶ በቁርጠኝነት የሚረጋገጥ የድርጊት እርሾ ነው፡፡ ለመወሰን ስንነሳም ልንጋፈጣቸው የሚገቡ ልዩ ልዩ ተግዳሮቶች መኖራቸውን መገንዘብ ይገባል፡፡ ከእነዚህም መካካል፡-

ጊዜያዊ ሕመሞች፡- በራችንን ከፍተን ያስገባናቸው ክፉ ነገሮች ወደ ሱስነት ከተቀየሩ በኋላ ዳግም በራችንን ከፍተን ውጡልን ብንላቸው በቀላሉ አይወጡም፡፡ በገቡበት ወቅት ቀስ በቀስ የተቆጣጠሯቸውን ቦታዎች በዋዛ የሚለቁ አይሆኑም፡፡ ወንበዴ የተቆጣጠራቸውን ሥፍራዎች መንግሥት አስገድዶና አስፈላጊውን መሥዋዕትነት ከፍሎ እንደሚያስለቅቅ ሁሉ እነዚህም በቆራጥ ውሳኔ ተገደው እንዲወጡ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ወንበዴ ለጊዜው የተቆጣጠረውን አካባቢ አጠፋፍቶና አውድሞ እንደሚሄድ ሁሉ ሱሶችም የተቆጣጠሩትን ሰውነት አካላዊና ኅሊናዊ ጉዳት ስለሚያደርሱበት በለቀቁትም ጊዜ ክፍተቱን መልካም ነገሮች ተቆጣጥረው እስኪሞሉትና ሰውነት እስኪያገግም ድረስ መጠነኛና ጊዜያዊ ሕመሞችና ድብርት እንደሚኖር መረዳት ይገባል፡፡

ተአማኒነት ማጣት፡- በክፉ የሱሰሰኝነት ሕይወቱ ያውቁትና ይሸሹት የነበሩት የትምህርት ቤት ወይም የሥራ ጓደኞች፣ ቤተሰቦችና ልዩ ልዩ የማኅበረሰቡ አባላት ወደ ቀደመ ማንነቱ የተመለሰውን ሰው ፈጥነው ላያምኑት ይችላሉ፡፡ እንደ አንዳንድ ክፉ ጓደኛ ቀርቦ ሊያጠምዳቸው መስሏቸው ሊሸሹትም ይችላሉ፡፡ ይህ ችግር ጊዜያዊ ስለሆነ ሳትቀየምና ተስፋ ሳትቆርጥ የጀመርከውን ከሱስ የመላቀቅ ጉዞ በፍጥነት ወደፊት መገስገስ ይኖርብሃል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ይህን በማስመልከት ሲያጽናናን “በቅንነትና እግዚአብሔርን በመፍራት ግብራችሁን አሳምሩ፤ ሥራችሁን ክፉ አስመስለው የሚያሙአችሁ ሰዎች ቢኖሩ ስለ ክርስቶስ ከምትሠሩት ከሥራችሁ ደግነት የተነሣ የሚያሙአችሁ ሰዎች ያፍሩ ዘንድ፡፡” (፩ኛጴጥ. ፫፥፲፮) እንዳለው፡፡

የክፉ ጓደኞች ተቃውሞ፡- በክፉ ምክራቸው ሰዎችን እየጎተቱ ወደ ጥፋት የሚከቱ ሰዎችና በእነርሱም ላይ አድሮ ይህን የሚያሠራቸው ሠይጣን አንድ ሰው ወደ መልካምና ክርስቲያናዊ ሕይወቱ ሲመለስ ዝም ብሎ የማየት ትዕግሥት አይኖራቸውም፡፡ ስለዚህም ያ ሰው ፍላጎቱንና ውሳኔውን እንዳያሳካ ለማድረግ የቻሉትን ሁሉ ይፈጽማሉ፡፡ ቢችሉ መጀመሪያውኑ እንዳይወጣ፣ አለበለዚያም ከወጣ በኋላ ተልፈስፍሶ ወደ እነርሱ እንዲመለስ ለማድረግ የማይፈነቅሉት ድንጋይ. የማቆፍሩት ጉድጓድ አይኖርም፡፡ አሁንም ቅዱስ ጴጥሮስ ይህን በማስመልከት እንዲህ ይለናል፡፡ “የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃችኋልና ዝሙትን፣ ምኞትን፣ ስካርን ወድቆ ማደርን፣ ያለ ልክ መጠጣትን፣ ጣዖት ማምለክን፡፡ እንግዲህ ዕወቁ ወደዚህ ሥራ አትሩጡ፤ ከዚህ ጎዳና ልክ መጠን ከሌለው ከዚያ ሥራም ተለዩ፤ እነሆ ከእነርሱም መካከል ሰዎች ስለ እናንተ ያደንቃሉ፤ በዚያ በቀድሞው ሥራ ሳትተባበሩዋቸው ሲያዩአችሁም ይሰድቡአችኋል፡፡” (፩ጴጥ. ፫፥፬) ይህን በማወቅ አንተም ምንም ዓይነት መከራ ቢያመጡብህ ወደ ኋላ ላለመመለስ መወሰን አለብህ፡፡

ለ. ሳያቅማሙ መፈጸም

ውሳኔ ብቻውን ምንም ያህል የተጠናና ያማረ ቢሆንም እንኳ ምንም ፋዳ አይኖረውም፡፡ የብዙዎቻችን ችግር የመወሰን ሳይሆን የመተግበር ሆኖ ነው የሚገኘው፡፡ ውሳኔህን ወደ ተግባር ለመለወጥ ሳትነሣሣም በቀጥታ የታሰርክባቸውን የሱስ ገመዶች ሁሉ በጣጥሰህ መጣል እንዳለብህ አትዘንጋ፡፡ ከሱስ እንዳትወጣ የሚፈልጉ አዛኝ የሚመስሉ ክፉ ጓደኞች “በአንድ ጊዜ ስለሚከብድህ ቀስ በቀስ እያስታመምክ ለመተው ሞክር“ ሊሉህ ይችላሉ፡፡ ይህ ግን የማዘናጊያ መንገድ እንጂ ሁነኛ መፍትሄ ኤደለም፡፡ የሚከተሉትን ነጥቦች በወጉ በመረዳትና በመጽናናት የተያዝክበትን የሱስ መረብ መበጣጠስ ብቻ ሳይሆን ወደዚያ የሚወስዱ የተለያዩ መንገዶችን ሁሉ መዝጋት ይኖርብሃል፡፡

ሰው ክቡር ፍጡር መሆኑን መረዳት፡- ሰው በትነት ተፈጥሮ በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ የተፈጠረ፣ በበደሉ ክብሩን ቢያጣም ወልደ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ ወደ ቀደመ ክብሩ የመለሰው የፍጥረታት ቁንጮ ነው፡፡ ለባዊት፣ ነባቢትና ሕያዊት ነፍስ ስላለችውም በባሕርይው ዐዋቂ ሆኖ የተፈጠረ፣ የልጅነትን ጸጋ በጥምቀት በተቀበለ ጊዜም ሁሉ ኃጢአትን የሚቃወምበት ኃይልና ጸጋ የተጨመረለት ክቡር ፍጡር ነው፡፡ በዚህም የተነሣ ከመጀመሪያዋ ጀምሮ ለርኩሰት ሳይሆን ለቅድስና ጠርቶናል፡፡ (፩ኛተሰ. ፬፥፯) ሁሉ ቢፈቀድልንም ሁሉ እንደማይጠቅመንና አንዳች ሊሰለጥንብን እንደማይገባ አስተምሮናል፡፡ (፩ኛ ቆሮ. ፮፥፲፪፤ ፲፥፳፫) ቅዱስ ዳዊትም “ሰውስ ክቡር ሆኖ ሳለ አላወቀም፣ ልብ (ማስተዋል) እንደሌላቸው እንስሶች ሆነ፣ መሰላቸውም፡፡” (መዝ. ፵፰፥፳) እንዲል፡፡

እግዚአብሔርን ማወቅ፡- ይህን ስንል በባሕርይው ሳይሆን በገለጠልን መጠን ከቅዱሳት መጻሕፍትና ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ቀርቦ ዐቅም በፈቀደ መረዳት ማለታችን ነው፡፡ ፈቃዱን፣ ሀልዎቱን ምሉዕነቱን፣ከሀሊነቱ፣ ሁሉን ቻይነቱን፣ ፍቅሩን፣ ወዘተ ባወቅን ቁጥር ወደ እርሱ የምንቀርብ እንሆናለን፡፡ ከዚያም የሚገዛን፣ የሚያዘንና የሚቆጣጠረን ሱስ ሳይሆን አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር ይሆናል፡፡ በሃይማኖት መኖራችንን ዓለማ የምናስተውለውና አምነን የምንታመነው ያኔ ነው፡፡ እንዲህ ከሆነም ከእግዚአብሔር ከአንተ ጋር ስለሚሠራ የሚያሸንህፍ ምንም ዓይነት ቁሳዊ፣ ምናባዊና መንፈሳዊ ጠላት ሊኖር እንደማይችል እርግጠኛ ሁን፡፡

ምክንያተኝነትን ማራቅ፡- ምንም እንኳን ለገጠሙን ችግሮች ልዩ ልዩ ምክንያቶችን መደርደር ብንችልም ዋነኛው ተጠያቂዎቹ ግን እኛው ራሳችን ነን፡፡ ለመውጣትም በምናደርገው ትግል ዋነኞቹ ተጋዳዮች እኛው ነን፡፡ በራሳችን ጣፋት ለገጠሙን ለሚገጥሙን ችግሮች ክሳችን ውጪ ሌሎችን ተጠያቂ ለማድረግ መሞከር ከኅሊና ወቀሳም ሆነ ከእግዚአብሔር ፍርድ እንደማድን ማወቅ ዐዋቂነት ነው፡፡ በተጨማሪም ተሸናፊነትን አርቆ እችላለሁ፤ እግዚአብሔር ይረዳኛል፣ ብሎ ችግሩን መጋፈጥ ራስን በመግዛት ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ ያስችላል፡፡

ስለዚህ ውድ ወንድማችን የሕያው እግዚአብሔር ማደሪያ መሆንህ (፩ቆሮ. ፫፥፲፮) ኃልን በሚሰጥ በክርስቶስ ሁሉን እንምችል እና በእርሱ ከአሸናፊዎች እንደምትበልጥ ማመን ይኖርብሃል፡፡ (ፊል. ፬፥፲፫፤ ሮሜ ፰፥፴፯-፴፱) ከሱሶች ስትለያይ ከሱሰኛ ጓደኞችህም መለያየት እንደሚኖርብህ አትርሳ፡፡ በእነርሱ ምትክ መንፈሳውን ጓደኞች በመተካት፣ ጸበል በመጠመቅ፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን በመገስገስና ንስሓ አባት ይዘህ ንስሓ በመግባት፣ ራስህን ለመንግሥተ ሰማያት ማዘጋጀት ይኖርብሃል፡፡ ከቃለ እግዚአብሔር ባለመራቅ እና ወደ ቅዱሳት መካናት ከክተርስቲያን ወንድሞችና እኅቶችህ ጋር በመጓዝ የቅዱሳንን በረከት ለማግኘት መትጋት አለብህ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን በተመለከተ “ብልቶቻችሁ ዓመፃ ሊያደርጉ ለርኩሰትና ለዓመፃ ባሪያዎች አድርጋችሁ እንዳቀረባችሁ እንደዚሁ ብልቶቻችሁ ሊቀደሱ ለጽድቅ ባሪያዎች አድርጋችሁ አሁን አቅርቡ፡፡” (ሮሜ፮፥፲፱) በማለት ያስተማረን ቃል የሕይወትህ መመሪ\ በማድረግ እንድትመላለስ እንመክርሃለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር