ቅዱስ መስቀል

በዲ/ን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰቅሎበት የነበረው መስቀል ያደርግ የነበረው ተአምራት በመቃወም አይሁድ እንደቀበሩት በአብዛኛዎቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ይተረካል፡፡ አይሁድ በሮማውያን ላይ እስከአመጹበት፣ ኢየሩሳሌም ከክርስትና በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ እስከጠፋችበት እስከ ፸ ዓ.ም ድረስ መስቀሉ በክርስቲያኖች እጅ ነበር፡፡ ይህም ቆስጠንጢኖስ ለኢየሩሳሌሙ ኤጲስ ቆጶስ ለአቡነ መቃርዮስ በጻፈው እና እነ አውሳብዮስ መዝግበው ባቆዩት የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ተገልጧል፡፡ ቀጣዮቹ ፫፻ ዓመታት ለክርስቲያኖች የመከራ ጊዜያት ነበሩ፡፡ በእነዚህ ጊዜያት የሮም ቄሣሮች ክርስቲያኖችን የሚያሳድዱባቸው ዓመታት ስለነበሩ መስቀሉን የመፈለግ ጉዳይ በልብ ይታሰብ እንጂ በተግባር ሊሞከር አልተቻለም፡፡

መስቀሉና ንግሥት ዕሌኒ

ጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች መስቀሉን ከጠፋበት (ከተሰወረበት) ያገኘቸው ንግሥት ዕሌኒ መሆኗን ይገልጻሉ፡፡ ድርሳነ መስቀል ዘየካቲት እና ዘመጋቢት እንደተገለጸው እስከ ፫፻፲፰ ዓ.ም ተሰውሮ የነበረው መስቀል ያለበትን ይገልጽላት ዘንድ አስቀድማ እግዚአብሔርን በጸሎት ጠየቀች፡፡ ከዚያም በሮሜ ሀገር የሚኖሩ ሊቃውንትንና ጥበበኞችን ሰብስባ የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበትን መሰቀል ዜና ንገሩኝ አለቻቸው፡፡ ሊቀ ጳጳሱ ቀራንዮ በሚባል ቦታ አዳምና ልጆቹን ለማዳን የክብር ባለቤት ጌታችን እንደ ተሰቀለ፣ በጎልጎታም እንደተቀበረ፣ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሳ፣ በዐርባ ቀንም በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ እንደ ዐረገ ተረከላት፡፡ ንግሥት ዕሌኒም ፈጽሞ ደስ አላት፣ የእግዚአብሔርን ፈቃድ እየጠየቀች ሰባት ዓመት ያህል ቆየች፡፡ ከሰባት ዓመት በኋላም ልጅዋ ቆስጠንጢኖስን በመንግሥቷ ዙፋን አስቀምጣ የክብር ባለቤት የኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል ትፍልግ ዘንድ ከሮም ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች፡፡ በ፫፻፳፭ ዓ.ም አየሩሳሌም ደርሳ አይሁድንም ሰብስባ የክብር ባለቤት የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ያለበትን ንገሩኝ፣ አባቶቻችሁ ወዴት እንደቀበሩት አሳዩኝ አለቻቸው፡፡ እነርሱ ግን እኛ የሆነውን አናውቅም፣ አባቶቻችንም መስቀሉን በምድር ውስጥ አልቀበሩም፣ ነገር ግን ስማቸው ኪራኮስ እና አሚኖስ የሚባሉ ሁለት አረጋውያን በእኛ ዘንድ አሉ፡፡ እነርሱም ስለዚህ ጉዳይ ይነግሩሽ ዘንድ ጠይቂያቸው አሏት፡፡

ንግሥት ዕሌኒ ወደ ቤተልሔም ገብታ “የታላቁ ንጉሥ ሀገሩ ቤተልሔም ሆይ ሰላምታ ይገባሻል” እያለች የመስቀሉን ነገር ይገልጽላት ዘንድ ለሰባት ቀናት እያለቀሰች ወደ እግዚአብሔር በመስገድ ማለደች፤ ጸለየች፡፡  ከዚያም ወደ ዮርዳኖስ፣ ቆሮንቶስ፣ ደብረ ታቦር፣ ቀራንዮ፣ ጌቴ ሴማኒ ሔዳ ሰባት ቀን ጾመች፣ ጸለየች፣ በጎልጎታ ድንኳኖቿን ተክላ ከተመች፡፡ በጾምና በጸሎት ብዙ ዕንባ በማፍሰስ እስከ ዐርባ ቀን ቆየች፡፡

በመጨረሻም በአረጋዊው ኪራኮስ አመላካችነት፣ በዕጣን ጢስ ጠቋሚነት ክቡር መስቀሉን ፈልጎ ለማግኘት ቁፋሮው ከመስከረም ፲፯ እስከ መጋቢት ፲ ቀን ወደ ስድስት ወራት የሚጠጋ ጊዜ ፈጀ፡፡ በመጨረሻም መጋቢት ፲ ቀን መስቀሉ ከተቀበረበት ወጥቷል፡፡ በዚህም መሠረት የኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ዕለቱን ታከብረዋለች፡፡

ቅዱስ መስቀሉና ኢትዮጵያ

ግማደ መስቀሉን ካገኙትና ከጠበቁት ሀገሮች ኢትየጵያ ሀገራችን አንዷ ናት፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መዛግብት እንደሚገልጹት ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮጵያ ጉዞ የጀመረው በ፲፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ሲሆን፣ በግሸን አምባ የተቀመጠው ደግሞ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመን መንግሥት ነው፡፡

በዐፄ ሰይፈ አርእድ ዘመነ መንግሥት በግብፅ ሡልጣን እና በኢትዮጵያ ንጉሥ መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት አንድ የልኡካን ቡድን ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ነበር፡፡ የልኡካን ቡድኑ መሪ የኢየሩሳሌሙ ፓትርያርክ አባ ዮሐንስ ነበሩ፡፡ ልኡካኑ ወደ ኢትዮጵያ ሲደርሱ የዐፄ ሰይፈ አርእድ ልጅ ዐፄ ዳዊት የኢትዮጵያ ንጉሥ ሆነው ነበር፡፡ ፓትርያርኩ በሁለቱ ሀገሮች መካከል የነበረውን ችግር በውይይትና በስምምነት ፈትተው አስማሟቸው፡፡ ዐፄ ዳዊት በነበራቸው ቀና መንፈስ አቡነ ዮሐንስ የኢየሩሳሌሙ ፓትርያርክ ዕሌኒ ንግሥት አስቆፍራ ካስወጣቸው ከጌታ መስቀል ክፋይ ለበረከት እንዲልኩላቸው ወርቅ፣ አልማዝ ሌላም የከበረ ማዕድን ገጸ በረከት አስጭነው ወደ ኢየሩሳሌም መልእክተኞችን ላኩ፡፡ መልእክተኞቹ ኢየሩሳሌም ደርሰው ገጸ በረከቱን ለፓትርያርኩ ከሰጡ በኋላ ፓትርያርኩ የጌታችንን ግማደ መስቀል የቀኙ ክፋይ ከሌሎች ንዋየ ቅድሳት ጋር ላኩላቸው፡፡

ግማደ መስቀሉ በግብፅ በኩል ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት በግብፅ ሡልጣን እና በንጉሥ ዳዊት መካከል ለኢትዮጰያውያን ተሳላሚዎችና ለነጋዴዎች ጥበቃ ማድረግን ጭምር የሚያካትት ስምምነት አካሔዱ፡፡ ግማደ መስቀሉን የያዙት የዐፄ ዳዊት መልእክተኛችም ያለ ችግር ወደ ኢትዮጵያ ጉዞአቸውን ቀጠሉ፡፡ ነገር ግን ዐፄ ዳዊት መልእክተኞቹን ለመቀበል ሲሔዱ መንገድ ላይ መሞታቸውን የጥቅምት ፱ ቀን ፲፬፻፬ ዓ.ም ታሪካቸው ይናገራል፡፡ ያን ጊዜ ግማደ መስቀሉ በሱዳን ስናር በሚባል ቦታ ነበር፡፡

ግማደ መስቀሉ ኢትዮጵያ የገባው መስከረም ፲ ቀን ሲሆን ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ግሸን አምባ ላይ ያስቀመጡት መስከረም ፳፩ ቀን በወሎ ክፍለ ሀገር ግሸን ደብረ ከርቤ ተራራ ላይ ነው፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የካቲት ፳፻፭ ዓ.ም

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎቻችን እንኳን በደህና መጣችሁልን!

የተወደዳችሁ በተለያዩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የምትማሩ ኦርቶዶክሳውያን ወንድሞቻችንና እህቶቻችን፤ እንኳን ለ2012 ዓ.ም የትምህርት ክፍለ ጊዜአችሁ በሠላም አደረሳችሁ፤ እንኳንም በደህና መጣችሁልን!

ዘመኑ የሰላም፣ የጤና እና የውጤታማነት እንዲሆንላችሁ እየተመኘን መንፈሳዊ መልእክቶቻችንን በተለመዱት ሚዲያዎቻችን (ጉባኤ ቃና፣ ድረ ገጽ http://gibi.eotcmk.org/a/ (አማርኛ) http://gibi.eotcmk.org/ao/ (Afaan Oromoo) እና ፌስ ቡክ https://www.facebook.com/የግቢ-ጉባኤያት-አገልግሎት-ማስተባበሪያ-ገጽ-Gibi-Gubaeyat-Coordination-414397429324567/ ላይክ በማድረግ) እንድትከታተሉ ለመጠቆም እንወዳለን!

ማኅበረ ቅዱሳን፣ የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ
ጥቅምት 05 ቀን 2012 ዓ.ም

Barattootni Yaa’iiwwan Mooraa Baga Nagaan Nuuf Dhuftan!

Dhaabbilee ol’aanoo addaddaa keessaatti barachuuf kan dhuftan ijoolleen Ortodooksii hundi keessan baga bara barnootaa 2012’n isin gahe; baga nagaan nuuf dhuftan!!! Akkuma kanaan duraa ergaalee afuurawoo keenya karaa miidiyaalee keenyaa (Gubaa’ee Qaanaa, Websaayitii http://gibi.eotcmk.org/a/ (አማርኛ) http://gibi.eotcmk.org/ao/ (Afaan Oromoo) fi FB keenya https://www.facebook.com/የግቢ-ጉባኤያት-አገልግሎት-ማስተባበሪያ-ገጽ-Gibi-Gubaeyat-Coordination-414397429324567/ waan isiniif dabarsinuuf LIKE gochuudhaan akka nu hordoftan isin yaadachiisna!

Waldaa Qulqullootaa, Qindeessaa Tajaajila Yaa’iiwwan Mooraa

Onkololeessa 05, B.A 2012

የሕማማት ሣምንት ሐሙስ ስያሜዎች

በሰሙነ ሕማማት ውስጥ ማለትም ከሰኞ አስከ ቅዳሜ 6 ቀናት ያሉ ሲሆን በተለይ ዕለተ ሐሙስ በተለያዩ ስያሜዎች ትታወቃለች፡፡ የተወሰኑትንም ለማየት ያህል ፡-

ጸሎተ ሐሙስ፡- የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋን የተዋሐደ አምላክ መሆኑን ለመግለጥና ለአርአያነት ጠላቶቹ መጥተው አስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ ያደረበት ነውና ጸሎተ ሐሙስ ተባለ፡፡ማቴ 26 ፡1

ሕፅበተ እግር፡- ጌታችን በዚህ እለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በፍጹም ትሕትና ዝቅ ብሎ አጥቧል፡፡ ይህም የሚያሳየው የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ መሆኑን ነው፡፡ ይህንኑ ለመዘከርም ዕለቱ ‹‹ሕፅበተ እግር›› ይባላል፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ከቅዱስ ፓተርያርኩ ጀምሮ ካህናት ሊቃነ ካህናት የደብር አስተዳዳሪዎች፤ በዕለቱ የተገኙትን ምእመናንን እግራቸውን በወይንና በወይራ ቅጠል ያጥባሉ፡፡

የምስጢር ቀን፡- ከሰባቱ ምሥጢራት አንዱ በዚህ ዕለት ተመሥርቷል፡፡ ይኸውም ‹‹ሲበሉም ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ ባረከ ቈርሶም ለደቀ መዛሙርቱ ሰጠና ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው፤ እንካችሁ፥ ብሉ፡፡ ጽዋውንም አንስቶ አመሰገነ፣ ይህ ስለ እናንተ ነገ በመስቀል የሚፈርስ የሐዲስ ኪዳን ደሜ ነው፥ ከእርሱም ጠጡ›› (ማቴ.26፡26) በማለት እኛ ከእርሱ ጋር፣ እርሱም ከእኛ ጋር አንድ የምንሆንበትን ምሥጥር ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ሥያሜ ነው፡፡ ይህንኑ አብነት በማድረግም በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሐ ታጥቦ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል ይዘጋጃል፡፡

የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ፡- ዕለቱ በዚህ ስያሜ የተጠራበት ምክንያት በዘመነ ኦሪት በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ነው፡፡ ‹‹ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን ሐዲስ ኪዳን ነው፤ ከእርሱ ጠጡ›› በማለቱ ይታወቃል፡፡ ሉቃ.22፡20

የነጻነት ሐሙስ፡- የሰው ልጅ ለኃጢአትና ለዲያብሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱ፣ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡ ጌታችን ስለ ሰው ልጅ ነጻነት ሲናገር ‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም ባርያ ጌታው የሚደርገውን አያውቅምና፡፡ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ›› (ዮሐ.15፡15) በማለት ከባርነት ወጥተን ልጆች የተባልንበት፣ ባርነት ርቆ ከእግዚአብሔር ጋር የተወዳጀንበት፣ ታርቀን አንድ የሆንበት፣  ፍቅር አንድነት ልጅነት የታወጀበት፣ ወደ ቀደመው ክብራችን የተመለሰንበት ዕለት በመሆኑ የነጻነት ቀን ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ከዕለተ ሐሙስ በትሕትና ራስን ዝቅ ዝቅ በማድረግ ከትዕቢትም መጠበቅን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን፣ በጎነትን፣ ለሰዎች ድኅነት መልካም ማድረግን፣ ትዕግስትን፣ በአገልግሎት ላይም በጾም በጸሎት እና በንሰሐ ሕይወትን መምራት፣ መተሳሰብንና ለሎችም መኖር እንዳለብን እንማራለን፡፡ ቀኑን አስበን ከቀኑም በረከትን እንድናገኝበት በዓሉንም ለሕይወት፣ ለድኅነት እና ለበረከት እንዲያደርግልን የእርሱ መልካም ፈቃድ ይሁንልን አሜን ፡፡

ምንጭ ፡- ስምዐ ተዋሕዶ ልዩ እትም ዘሰሙነ ሕማማት ከሚያዝያ 1-15 ቀን 2004 ዓ/ም

ሰሚ ያጣው የሕፃናት ጩኸት

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

ቀኑ ወረፋውን ለጨለማው ለመልቀቅ በማመናታት ላይ ያለ ይመስላል፡፡ የአዲስ አበባ ምድርም የፀሐይን ብርሃን በሰው ሠራሽ ብርሃን ለመተካት ፓውዛዎቿን ስልም ቁልጭ እያደረገች ነው፡፡ ሁሉም በየፊናው እየተሯሯጠ ነው፡፡ ጠዋት ሥራ የገባው ወደ ቤቱ ለመመለስ፣ ማታ የሚሠራው ደግሞ በአዲስ መንፈስ ለመሥራት ጥድፊያ ላይ ነው፡፡

ከዐዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ ተነሥቼ በድካም የዛለ ሰውነቴን ለማሳረፍ ወደ ቤቴ እያመራሁ ነው፡፡ ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ፊት ለፊት ዋናውን አስፓልት አቋርጬ ቀጥታ በድባብ መናፈሻ አድርጌ የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ግቢን ትቼ ወደ ታች ስታጠፍ በርቀት የሚስረቀረቅ የሕፃናት ኅብረ ድምፅ ሰማሁ፡፡ ምን እንደሚሉ አይሰማም፤ የድምፃቸው ጣዕመ ዜማ ግን ልብን ሰርስሮ ይገባል፡፡

Read more

በፍቅር መኖር

…በመ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ…

በክርስቲያናዊ ሕይወት ለመኖር የወሰነ ሰው ሰውን ሁሉ ሊወድ ይገባል፡፡ ፍቅር ሲባል ፍትወታዊ የጾታ ፍቅር ሳይሆን ሁሉንም ሰው ሳይለያዩ መውደድ ነው፡፡ ለዚህ ነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሕግጋት ሁሉ ፍቅርን ያስበለጠው፡፡ (ዮሐ. 15፥12) ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲጠቅስ በሰዎችና በመላእክት ልሳን ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ  ናስ ወይም እንደሚንሿሿ ጸናጽል ሆኛለሁ፤ ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና ዕውቀትን  ሁሉ ባውቅ ተራሮችንም እስካፈርስ ድረስ እምነት ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ፤ ድሆችን ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል፤ አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም፡፡ ፍቅር ይታገሣል፤ ቸርነትም ያደርጋል፤ ፍቅር አይቀናም፤ ፍቅር አይመካም፤ አይታበይም፤ የማይገባውን አያደርግም…(1ኛ ቆሮ. 13፥1) በማለት አስረድቷል፡፡

Read more