ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል ሁለት

በዲ/ን መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

የጾም ዓይነቶች

የጾም ዓይነቶች ሁለት ናቸው እነርሱም የአዋጅ እና የፈቃድ በመባል ይታወቃሉ፡፡

ሀ. የዐዋጅ ጾም

የዐዋጅ ጾም የሚባሉት በዐዋጅ ለሁሉም ሰው ማለት ከሰባት ዓመት በላይ ለሆነ ሰው ሁሉ የሚታወጅ እና በይፋ ሁሉም ተባብሮ ስለሚጾማቸው ነው፡፡ “በጽዮን መለከትን ንፉ፥ ጾምንም ቀድሱ፥ ጉባኤውንም አውጁ፥” (ኢዩ ፪፥፲፭) እንደተባለ አንዴ በቤተ ክርስቲያን ታውጆ ሥርዓት ተሠርቶለት የሚጾም ስለ ሆነ የአዋጅ ጾም ይባላል፡፡ የአዋጅ ጾም በማለት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምታውጃቸው እና ሁላችን በጋራ የምንጾማቸው አጽዋማት ሰባት ሲሆኑ እንደሚከተለው እንመለከታቸዋለን፡-

  1. ዓቢይ ጾም (ጾመ ሁዳድ)
  2. ጾመ ድኅነት (ዓርብ እና ረቡዕ)
  3. ጾመ ሐዋርያት (የሰኔ ጾም)
  4. ጾመ ፍልሰታ
  5. ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)
  6. ጾመ ነነዌ
  7. ጾመ ጋድ ናቸው፡፡

ለ. የፈቃድ ጾም

የፈቃድ ጾም የሚባለው ሁሉም ሰው በዐዋጅ ሳይታዘዝ በፈቃዳችን የምንጾማቸው ናቸው፡፡ በቀኖና የሚሰጠን ጾም የሚመደበው ከዚህ ውስጥ ነው፡፡ አንዳዴም በተለየ ሁኔታ ለራሳችን የምንጾመው ጾምም የፈቃድ ይባላል፡፡ ለምሳሌ ጾመ ዮዲት (ጳጉሜን ላይ የሚጾም) እና ጾመ ጽጌ የሚጾሙ አሉ፤ እኒህም የፈቃድ አጽዋማት ናቸው፡፡

ውድ ተማሪዎች ጾም ፍቅርን ለእግዚአብሔር መግለጫ በመሆኑ ከልባችን ወደነው መጾም ይገባል፡፡ በጾም ስሜትን ራስን እንገዛበታለን፡፡ ጾም መንፈሳዊ ኃይልን ታጎናጽፋለች፤ አጋንንትን ለማራቅ እጅግ ትጠቅመናለች እንዲሁም ለመንፈሳዊ አገልግሎት የበረታን ታደርገናለች እና በአግባቡ በመጾም የምታሰጠውን ዋጋ ለማግኘት እንትጋ፡፡

እንደ ግብዞች አትጠውልጉ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዴት መጾም እንዳለብን የተራራውን ትምህርት ባስተማረበት ወቅት እንዲህ በማለት ተናገሮ እንመለከታለን “ስትጦሙም፥ እንደግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮)። በዚህ ንባብ ግብዞች የሚለውን ቃል በሁለት መልኩ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስቀምጦት ይገኛል። እነዚህም፡-

 ፩. መጦመቸው እንዲታወቅላቸው ፊታቸውን የሚያጠፉ እንዲሁም ይጠወልጋሉ። እነዚህ ጦማቸውን ዋጋ ለሚከፍል እግዚአብሔር ከማሳየት ይልቅ ለሰዎች አድናቆት ለማግኘት ሲሉ ብቻ የጾምን ዓላማ ያጠፉታል።

፪. ሳይጾሙ እንደጾሙ የሚያስመስሉ ከንፈራቸውን የሚያደርቁ ግብዝ ተብለው ተጠርተዋል። የምንጾመው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረትን ለማድረግ ነው እንጂ ውዳሴ ከንቱን ለማግኘት አይደለም፤ በሁለቱም መልክ የተገለጡት ግብዞች ግን የጾምን ዓላማ የረሱና ያልተገነዘቡ ናቸው። በግብዝነት የሚገኘው ደስታ ጊዜያዊና ወዲያው የሚረሳ ነው ሆኖም ቅጣቱ ከባድ መሆኑን ዐውቆ መጠንቀቅ ይገባል።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በተለይ በልቶ ማስመሰል ውዳሴ ከንቱን መፈለግ ብቻ ሳይሆን ውሸትንም በውስጡ የያዘ ነውና ከግብዝነት በመራቅ በእውነት ለጾም ሕግና ሥርዓት ልንገዛ ይገባል። ለቤተሰብ ለጓደኛ ለቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ራሳችንን በውሸት ሕጋዊ አድርገን ለማሳየት ስንል መንግሥተ እግዚአብሔርን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይገባል። ለሰው ጾመኛ ከመምሰል በመታቀብ ዋጋ ለሚከፍለው ጌታ ራስን ማሳየት ያስፈልጋል። ፊትን በማጥቆር ከመጾም ፊትን ከእግዚአብሔር የሚያገኙትን ዋጋ በእምነት በተስፋ በመጠበቅ ብሩህ ማድረግ በእጅጉ ይገባል። ጌታችን ጾሞ እንዴት መጾም እንዳለብን አስገንዝቦናል በዚያው መሠረት በመጾም ሥርዓትን ልንፈጽም ይገባል።

ክርስቶስ አምላካችን ዐርባ ቀንና ሌሊት በመጾም ጾም የመልካም ሥራ መጀመሪያ እንድትሆን ሰጥቶናል። እኛም የሐዋርያቱን ትውፊትና ኑሮ መሠረት በማድረግ ያማረ የጾም ሕግን ከትውልድ ትውልድ እንቀባበለዋለን። ጌታችን የጾመው በቁዔት አገኝበታለሁ ብሎ ሳይሆን አጋንንትን፣ የኃጢአት ሥሮች የተባሉ ትዕቢት፣ ስስት እና ፍቅረ ነዋይን የምናሸንፍበትን ሕግ ሊሠራልን እና ተግባሩን ሊያመለክተን ነው እንጂ ጾማችሁን ሁሉ ጾሜላችኋለሁ ከዚህ በኋላ መጾም አይጠበቅባችሁም ለማለት አይደለም።

የተወደዳችሁ ተማሪዎች በግቢ ሕይወታችሁ ከብዙ ማኅበረሰብ ጋር እንደመኖራችሁ በሃይማኖት ከማይመስሉን በተለይ ከመናፍቃን ጥያቄ ሊቀርብልን ይችላል። ለምሳሌ አጽዋማት ለድኅነት አያስፈልጉም አንዴ ክርስቶስ ጾሞልናል፤ በዚህ ጊዜ እንድትጾሙ የተጻፈው የት ነው? ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም የሚለውን ሕግ ጥሳችኋል ሊሉን ይችላሉ።

ውድ ተማሪዎች ከመናፍቃን ጋር ያለን ልዩነት ሰፊና የመዳናችን መንገድ ላይ መሆኑን ልብ ማለት አለባችሁ ይህ ማለት ከላይ የጠቀስነው ንግግራቸው የሚመነጨው እምነት ብቻ ከሚለው አስተምሮአቸው ነው። ምግባር ለድኅነት አያስፈልግም በጸጋው ብቻ ድነናል ከሚለው አቋማቸው መሆኑን በመረዳት ከእነርሱ መራቅ ሐሳባቸውን አለመስማት ይኖርብናል። ምክንያቱም ጾም ትእዛዘ እግዚአብሔር ናት፤ ምግባር የእምነት ነፍስ ናትና “መጽሐፍም፦ አብርሃምም እግዚአብሔርን አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቈጠረለት ያለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ። ሰው በእምነት ብቻ ሳይሆን በሥራ እንዲጸድቅ ታያላችሁ። … ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደ ሆነ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው።” (ያዕ. ፪፥፳፫-፳፮) እንደተባለ። እምነት ከምግባር ተዋሕዶ ሊገኝ ግድ ነው። እንግዲህ ከምግባራት ቀዳሚዋ ጾም መሆንዋ ደግሞ ሊዘነጋ አይገባውም። ጌታችን ስለ ሆድ ማሰብ ሞት እንደሆነ አስተምሮናል አስቀድመን ማሰብ የሚገባን ስለ ጽድቅ መሆኑንም አሳስቦናል “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፥ ይጠግባሉና።” (ማቴ. ፭፥፮)። “ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?” (ማቴ. ፮፥፳፭)።

ስለዚህ ክርስቶስ ጾሞልሃል የሚለውን የሰይጣን ትምህርት ትተን “ከመዝ ግበሩ፤ እንዲህ አድቡ” የሚለውን የክርስቶስን ድምጽ በመስማት የተወልንን የአርአያነት መንገድ በመከተል እውነተኛ በጎቹ ልንሆን ይገባል። “ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል።” (ማቴ. ፮፥፴፫) “ስትጦሙም፥ እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፤ ለሰዎች እንደ ጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋቸውን ተቀብለዋል።” (ማቴ. ፮፥፲፮።)  ‘ይህም ሁሉ’ የተባለው ምግብን እና መሰሎቹን ነው። ክርስቶስ አትጹሙ አላለም ስትጾሙ እንደ ግብዞች አትሁኑ በማለት አጿጿሙን ተናገረ እንጂ ስለዚህ ጾም ክርስቶሳዊ ትእዛዝ ነው።

ወደ አፍ የሚገባ አያረክስም በማለት ሆድን አምላክ በማድረግ ሊሾሙብን እንደ ሔዋን ራቁታችን ሆነን ገነትን መንግሥተ ሰማይን አጥተን እንዳንጠፋ መጠንቀቅ አለብን።  ውድ ተማሪዎች ተመልከቱ ጌታችን ስለ እጅ ንጽሕና ሲጨነቁ ስለ አመጋገብ ወጋቸው ከሕገ መጽሐፍ በላይ ሲያሳስባቸው ተመልክቶ የተናገራቸውን ነገር “እርሱም፦ እናንተ ደግሞ እንደዚህ የማታስተውሉ ናችሁን? ከውጭ ወደ ሰው የሚገባ ሊያረክሰው ምንም እንዳይችል አትመለከቱምን? ወደ ሆድ ገብቶ ወደ እዳሪ ይወጣል እንጂ ወደ ልብ አይገባምና አላቸው። እርሱም አለ፦ ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው። ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ ሐሳብ፥ ዝሙት፥ መስረቅ፥ መግደል፥ ምንዝርነት፥ መጐምጀት፥ ክፋት፥ ተንኰል፥ መዳራት፥ ምቀኝነት፥ ስድብ፥ ትዕቢት፥ ስንፍና ናቸውና፤ ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል ሰውን ያረክሰዋል።” (ማር. ፯፥፲፰-፳፫)። ተማሪዎች ተመለከታችሁን? ይህ ጾምን የሚያጸና እንጂ የሚሽር ነውን? አይደለም ምክንያቱም ጾም ማለት ከምግብና ከሚያረክሶ ነገሮች ሁሉ መራቅ ነው።

በአጠቃላይ ከመናፍቃን ራሳችንን እንጠብቅ በተዋበች የጾም ሕግ ጽድቅን እንፈልግ፤ ከተድላ ደስታ በመራቅ ከእግዚአብሔር ጋር አንድ እንሁን “ትእዛዙንም የሚጠብቅ በእርሱ ይኖራል እርሱም ይኖርበታል፤ በዚህም በእኛ እንዲኖር ከሰጠን ከመንፈሱ እናውቃለን።” (፩ኛዮሐ. ፫፥፳፬ እንደተባለ። በተጨማሪም ምሳሌውን አርአያነቱን በማስተዋል እንከተል “በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል።” (፩ኛዮሐ. ፪፥፮) ተብሎ እንደተጠቀሰ።

የአጽዋማትን ጊዜ የተመለከተውን ልንወዛገብበት አይገባም። ውድ ተማሪዎች የእኛ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሥርዓተ አምልኮ ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ አይደለም ይልቁንም የቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት፣ ትውፊትና ከሐዋርያት ጀምሮ ያሉ አበው ትምህርት ሕይወት እንደ ምንጭ የሚወሰድ በመሆኑ ከበቂ በላይ ማስረጃ አለን። በሐዲስ ኪዳን ቀኖና ውስጥ ያሉ ስምንቱ መጻሕፍት ሁሉም ላይ የጾም ጊዜ ሥርዓት በቀኖናው ተጽፎ እንደሚገኝ መዘንጋት አይገባም።  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ማኅበረ ቅዱሳን ፲፫ኛውን የግቢ ጉባኤያት ዓለም አቀፍ ሴሚናር በማካሄድ ላይ ይገኛል

በመላው ዓለም የሚገኙና በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙ የግቢ ጉባኤያት ሥራ አስፈጻሚዎች፣ የስድስቱ ማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች፣ የማእከላትና የወረዳ ማእከላት የግቢ ጉባኤያት ዋና ክፍል ተወካዮች የሚሳተፉበት ፲፫ኛው የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ከየካቲት ፳፩-፳፫ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ድረስ በቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣን (በብሔራዊ ሙዚየም) በማካሄድ ላይ ይገኛል፡፡  

ዓርብ የካቲት ፳፩ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም በተደረገ አቀባበልም ከእጽበተ እግር ጀምሮ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ መ/ር ዋሲሁን በላይ እና የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ አጾ አበበ በዳዳ የእንኳን ደኅና መጣችሁ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

ቅዳሜ በነበረው መርሐ ግብርም በመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን ልዑካን በጸሎት ወንጌል የተጀመረ ሲሆን

የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር ጉባኤ አባል የሆኑት ዲ/ን ብንያም አያሌው በ፲፫ኛው የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ላይ ለተገኙ ተሳታፊዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር አድርገዋል። በዚህ ጉባኤ ትኩረት ከሚደረግባቸው ጉዳዮች መካካልም፡- የማኅበሩን ተቋማዊ ለውጥ አስመልክቶ በተለይም በግቢ ጉባኤያት የተደረጉ ማሻሻያዎችን ማስተዋወቅ፣ የአዲሱን ሥርዓተ ትምህርት አተገባበር እና የግቢ ጉባኤያት ድርሻ፣ በግቢ ጉባኤያት የመምህራን እጥረት ለመቅረፍ የተዘጋጀ ፕሮጀክት ላይ ተወያይቶ አቅጣጫ ማስቀመጥ እና ከተመረጡ ግቢ ጉባኤያት እና አባላት ልምድ ልውውጥ እንደሚደረግ ገልጸዋል፡፡

መርሐ ግብሩ ቀጥሎም በመ/ር ብርሃኑ አድማስ “አንተ ጎበዝ ተነሥ እልሃለሁ” (ሉቃ. ፯፥፲፬) በሚል ርእስ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲሆን የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ መምህር ዋስይሁን በላይ የሁለት ዓመት የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበዋል፡፡ ባቀረቡት ሪፖርትም፡- በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን ከቅዱስ ሲኖዶስ በብቸኝነትና በቀዳሚነት ከተሰጡት አገልግሎቶች አንዱ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት (ዩኒቨርሲቲና ኮሌጆች) የሚማሩ ኦርቶዶክሳዊያን ትምህርተ ሃይማኖት እያስተማረ ለአገልግሎት ማሰማራት ነው ብለዋል፡፡ ይህንንም ላለፉት ፴፫ ዓመታት በእግዚአብሔር ቸርነት ፣ ከቤተ ክርስቲያን አካላት ጋር በጋር ሲያከናውን መቆየቱንም ጠቅሰዋል፡፡

ማኅበሩ የግቢ ጉባኤ አገልግሎትን የሚመራበት ዓላማ ኦርቶዶክሳውያንና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን ሙሉ ሰብእናን የሚገነባ ሥርዓተ ትምህርት በማስተማር ዘመኑን የዋጁ ምሉዕ ኦርቶዶክሳዊ የሆኑ፣ በቤተ ክርስቲያን አስተዳዳራዊ መዋቅር የሚያገለግሉ፣ እንዲሁም በማኅበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊ በፖለቲካዊ እና በሀገረ አስተዳደር ጉዳዮች መሪ/ንቁ ተሳታፊ አገልጋዮችን ለማፍራት እና ለማሠማራት ነው ብለዋል፡፡

በአሁን ሰዓት በሀገር ውስጥ በሚገኙ ፫፲፭ ግቢ ጉባኤያት በመንግሥት ዩኒቨርስቲዎች እና ፩፻፶፪ ግቢ ጉባኤያት በግል ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ከ፩፻፷ ሺህ በላይ ተማሪዎች በተዘጋጀላቸው ሥርዓተ ትምህርት እየተማሩ ሲሆን በውጭ ሀገር በስድስት ማእከላት አንድ ግንኙነት ማእከል፣ ፲፰ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ላይ በቨርቹዋል ፲፬፻ በላይ ተማሪዎች እየተማሩ ይገኛሉ፡፡ በዚህም በአንድ ሳምንት ፳፻፶ የትምህርት መርሐ ግብር ተዘርግቶ ፳፻፶ መምህርን ተመድበው በማስተማር ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

መምህር ዋሲሁን ሪፖርታቸውን በመቀጠል፡-

  • የመማሪያ መጽሐፍትን ለተማሪዎች በጥራት አዘጋጅቶ በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውን፣
  •   የግቢ ጉባኤ መጽሐፍት ከ፲፱፻፺፰ ዓ.ም ጀምሮ በተዘዋዋሪ ጥብቅ ፈንድ የሚመራ ሲሆን የተዘጋጁትን   የኮርስ መጽሕፍት ፸፪ ሺህ ሰባት መቶ አሥራ ሰባት ኮፒ በአማርኛና በኦሮምኛ ቋንቋ ታትሞ ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ተሠራጭዋል።
  • ለግቢ ጉባኤያት ለሚገኙ ግቢ ጉባኤያት የንስሓ አባቶች እና አማካሪዎች ተከታታይ ዓቅም ማሳደጊያ ሥራ ተሠርቷል።
  • አዲሱ ሥርዓተ ትምህርት ላለፉት ሁለት ዓመታት በከፍተኛ ባለሙያዎች ነባሩን ሥርዓተ ትምህርት በመገምገም፣ በመንግሥት እየተተገበረውን ያለውን የሀገሪቱን አዲሱ ሥርዓተ ትምህርትና መልክ ከ፪፻፲፩ ጀምሮ ተዘጋጅቶ እየተተገበረ ያለውን የሰ/ት/ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት በማገናዘብ ተዘጋጅቷል።
  • ዘመኑን የዋጀ፣ አካታች፣ ሙሉ ሰብእና የሚገነባ፤ የግቢ ጉባኤ ምሩቃንን በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር፣ በማኅበራዊ፣ኢኮኖሚያዊ ፣ ፖለቲካዊ እና ሀገራዊ ጉዳዮችን ንቁ ተሳታፊ እና መሪ የሚያደርግ ሥርዓተ ትምህርት ተዘጋጅቶ በዚሁ ዓመት በ፳ ግቢ ጉባኤያት ትግበራ ተጀምራል፡፡
  • በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤ ለተመረጡ ፳፻፲፮ ተመራቂ ተማሪዎች እንደየዝንባሌያቸው ሀገራቸውንና ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲያገለግሉ የሚያግዛቸውና በማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር እና በሀገር አስተዳደር ተሳታፉ እንዲሆኑ የሚያስችላቸው አቅም ማጎልበቻ ሥልጠናዎች በባለሙያዎች ተሰጥቷቸዋል።
  • የማኅበሩ አባላት፣ የሰት/ቤት መምህራንና በየአጥበያው የሚገኙ መምህራን በተጨማሪ በግቢ ጉባኤያት የሚያስተምሩና የሚያሠለጥኑ እንዲሁም አገልግሎቱን የሚያስተባብሩ ፶፩ መደበኛ መምህራን እና የግቢ ጉባኤ አስተባባሪዎች በሙሉ ጊዚአቸው ተመድበው አገልግሎቱን እያፋጠኑ ይገኛሉ ።

ዋና ሥራ አስፈጻሚው በሪፖርታቸው ከዚህ በተጨማሪ በርካታ ሥራዎችን መሥራት እንደተቻለ በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን ከተሳታፊዎች ለቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ እንጦንስ የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በ፲፫ኛው ዓለም አቀፍ የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር መርሐ ግብር በመገኘት በሰጡት ቃለ ምእዳን “ማኅበረ ቅዱሳን ባይኖር ወጣቱን ማን ይይዝልን ነበር፡፡ በዚህ በ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን ወጣቱ ቤተ ክርስቲያኑን እንዲያውቅ ሀገሩን እንዲያገለግል እያደረገ ነው” ብለዋል፡፡

ከስዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብርም የማኅበረ ቅዱሳን ተቋማዊ ለውጥ በግቢ ጉባኤያት በተመለከተ በመ/ር ዋሲሁን በላይ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚና በአቶ ግዛቸው ሲሳይ የማኅበረ ቅዱሳን የሥራ አመራር አባል ቀርቦ ለቀረቡ ጥያቄዎችም ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በመቀጠልም ከአሜሪካ ማእከል የግቢ ጉባኤያት ተሞክርን አስመልክቶ የጆርጅ ማሰን ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ በሆኑት ማርያማዊት በርታ እና በመቅደላዊት መርሻ የቨርቱዋል ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ በቨርቹዋል ቀርቧል፡፡ የግቢ ጉባኤያት ሁለንተናዊ አገልግሎት ተሞክሮ በተመለከተም በዲ/ን ብርሃኑ ታደሰ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር አባል እና በአቶ አበባ በዳዳ የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ ቀርቦ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በምሽት በነበረ መርህ ግብር ላይ የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ትግበራም በተመረጡ ግቢ ጉባኤያት ቀርቦ በአቶ በቃሉ ለይኩን በሥራ ዘርፍ ከመሠማራት ቅድመ ዝግጅት ወይም የሲቪ አዘገጃጀት ቀርቦ የዕለቱ መርሐ ግብር ፍጻሜ ሆኗል፡፡

  

 

 

 

 

የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ለሚቀጥሉት ሦስት ቀናት ይካሄዳል

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤት አገልግሎት ማስተባበሪያ በሁለት ዓመት አንድ ጊዜ የሚያካሂደውን የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ከየካቲት ፳፩-፳፫ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ድረስ በቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣን (በብሔራዊ ሙዚየም) ያካሂዳል፡፡

በሴሚናሩ ላይ ልዩ ልዩ መርሐ ግብራት የሚከናወኑ ሲሆን ከአቀባበል ጀምሮ ትምህርተ ወንጌል፣ የማኅበረ ቅዱሳን ተቋማዊ ለውጥ በግቢ ጉባኤያት ፣ የግቢ ጉባኤያት ሁለንተናዊ አገልግሎት ተሚክሮ፣ የግቢ ጉባኤት አገልግሎት ትግበራ ተሞክሮ (በተመረጡ ማእከላት)፣ የቤተ ክርስቲን ፈተናዎችና የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት በተሰኙና በሌሎችም ዝግጅቶች ለሦስት ተከታታይ ቀናት ይቀጥላል፡፡

በመርሐ ግብሩም ከመላው ዓለም የተውጣጡ ከ፬፻፶ በላይ ተሳታፊዎች የሚገኙ ሲሆን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የግቢ ጉባኤያት የሥራ አስፈጻሚዎች፣ የስድስቱ ማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች፣ የማእከላትና የወረዳ ማእከላት የግቢ ጉባኤያት ዋና ክፍሎች ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ይገኛሉ፡፡   

ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ

ክፍል አንድ

በዲ/ን መብራቱ ስንታየሁ (ከአዳማ ማእከል)

ጾም ለሰውነት የሚያምረውን እና የሚያስጎመዠውን ነገር ሁሉ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ብሎ  መተው፣ ራስን በመግዛት ጣዕመ ዓለምን በመናቅ እግዚአብሔርን መከተል ማለት ነው፡፡ ጾም  ራስን ከክፉ ሥራዎች ሁሉ በማሸሽ የመንፈሳዊ ተጋድሎ መፈጸሚያ መሣሪያ እና የሥጋ ልጓም ነው፡፡ መንፈሳዊ በረከትን ለማግኘት ለትእዛዘ እግዚአብሔር ራስን ማስገዛት ነው፡፡ ፍጹም የሆነ የእግዚአብሔርን ርዳታ ማግኛ የፍቅር መንገድ ነው፡፡ ጾም ሃይማኖትን መግለጫ በተግባር ማሳያ መታመኛ መሣሪያ ነው፡፡ ጾም፤ ወዶ ፈቅዶ ምግብን በጊዜ ገደብ ጥሉላትን በቀናት/በወራት ገደብ እንዲሁም ነፍስን ከሚያሳድፉ ክፉ ሥራዎች መከልከል ነው፡፡ ለእግዚአብሔር ያለን ፍጹም ፍቅር የሚገለጠው በጾም በጸሎት እና ምጽዋት ነው፡፡ የቀና እና የተስተካከለ መንፈሳዊ ሕይወትን ከሚያደናቅፉ ማናቸውም እኩይ ተግባራት መራቅ እና መከልከል ጾም ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ነፍስን ሊያቆስላት የሚችለው ምንድን ነው? ስንል መልሱ የሥጋ ፈቃድን መፈጸም፣ በደል፣ ኃጢአት …ነው የሚል ይሆናል፡፡ ሰው ተማሪ ቢሆን ሠራተኛም ቢሆን በምንም ዓይነት ሥራ እና ሁኔታ ላይ ቢሆን ክርስቲያናዊ ሕይወቱን ለማረም ዕለት ዕለት መንፈሳዊ ተግባራትን መተግበር ያስፈልጋል፡፡ በይበልጥ ሐዋርያት የሥራ መጀመሪያ ያደረጓትን ጾምን እኛም አጥብቀን ልንይዝ ይገባል፡፡ “ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና፥ ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሰላም ነው።” (ሮሜ. ፰፥፮)፡፡ ሥራችንን ክርስቲያናዊ ጉዞአችንን ፍጹም የሚያደርግልን ጾም ነው፡፡ ለዚህም ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስን እንደ ምሳሌ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ስለዚህ ተማሪዎች ቀዳሚት ትእዛዝ የሆነች ሕግን ገንዘብ በማድረግ ሕይወታችንን ሰማያዊ ዋጋ በሚያሰጥ መልክ እንምራ፡፡

ጾምን ለምን እንጾማለን?

ጾም በመጀመሪያ ለሰው የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ የሰው ልጅ ቢመራበት የዘላለምን ሕይወት የሚወርስበት ልዩ የእግዚአብሔር የፍቅር ሕግ ነው፡፡ ሰው ፍትወቱን በዚህች ባማረች ሕግ ገዝቶ ዓይኑን ክፉ ከማየት፣ ጆሮውን ክፉ ከመስማት፣ ምላሱን ክፉ ከመናገር ከማማት፣ እግሩን እጁን ከመስረቅ ደም ለማፍሰስ ወደ ክፉ ከመገስገስ ቢከለክል ዋጋው ምንኛ ያማር ይሆን ነበር፡፡ እኛ በዚህ ዘመን ያለን ወጣቶች በዓለሙ ካለ ክፋት የትኛውን ተጸይፈን እንተዋለን? ዘመነኛው ቴክኖሎጂ ያመጣልንን ማኅበራዊ ሚዲያ በመጠቀም ክፉኛ ወደሚያቆስለን ለገሃነም ወደሚሰጠን የሥጋ ሥራ አዘንብለናል፡፡ ነገር ግን የተሰጠንን በጎ አእምሮ በመጠቀም ወደ ኃጢአት ከመሄድ ራሳችንን ልንጠብቅ እና ልናነጻ ይገባል፡፡ እስኪ አሁን ደግሞ የጾምን ጥቅም በቅደም ተከተል እንመልከት፡-  

፩. ኃይለ እግዚአብሔርን ለማግኘት

አብዝቶ መመገብ ፈቃደ ሥጋ በፈቃደ ነፍሳችን ላይ እንዲሰለጥን ሰፊ በር ይከፍታል፡፡ ፍትወታተ ሥጋ እንዲሰለጥኑብንም ዋነኛ ሞተራቸው በመሆን ይጠቀሳል፡፡ ጥጋብን፣ ትዕቢትን፣ ንዝህላልነትን፣ ዝሙትን በማምጣት መንፈሳዊ ፍሬን እንዳናፈራ ያግደናል፡፡ ሰዶምን በእሳት እንድትቃጠል ካደረጓት ምክንያቶች አንዱ እንጀራን መጥገብ እንደሆነ (ሕዝ. ፲፮፥፵፱) ተገልጧል፡፡ ፈቃደ ሥጋችን በፈቃደ ነፍሳችን ላይ ኃይል እንዳይኖረው ጾም መጾም እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ ነቢዩ ዳንኤል ከሦስቱ ሕፃናት ጋር ከኢየሩሳሌም ተማርከው ወደ ናቡከደነፆር ግዛት ከተወሰዱ ዕብራውያን ወጣቶች መካከል ተመርጦ ሦስት ዓመት በከለዳውያን ትምህርት ቤት የከለዳውያንን ጥንቆላ (ኮከበ ቆጣሪ)፣ ሕልም መፍታት፣ ቋንቋ እና ባህላቸውን ከሦስቱ ወጣቶች ጋር በመሆን እንዲያጠኑ በተቃራኒው ደግሞ የራሳቸው የሆነውን የእስራኤልን እምነት እና ባሕል እንዲረሱ በተደረጉበት ጊዜ ዳንኤል እንዲመገቡ የተፈቀዱላቸውን የንጉሡን ምግብ እና መጠጥ ከመብላት እንቢ አለ፤ የአሕዛብ ምግብ እንደሚያረክሰው አስቧልና፡፡ ይልቁንም ቆሎ እየበሉ ይማሩ እንደነበር ትንቢተ ዳንኤል ያስገነዝበናል፡፡

ሰውነታቸው ቅቤን በማጣት ቢነጣም ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸው ኅብረት በጣም ከፍተኛ ነበር፡፡ በጾም መጠንከራቸው በትምህርታቸው ጎበዝ እና በንጉሥ ፊት ሞገስ ያላቸው የሚመረጡ ከመሆን አላገዳቸውም፤ እንዲያውም ከሌሎቹ በላይ ሞገስ እንዲኖራቸው በሀገሪቱ ውስጥ ሥልጣን እንዲያገኙ፣ የተደበቀን ምሥጢር በመግለጥ የበረቱ እንዲሆኑ አደረጋቸው እንጂ፡፡ እግዚአብሔርም በነገር ሁሉ ይረዳቸውና ከጎናቸው ይሆንላቸው እንደነበረ መጽሐፍ ያስገነዝበናል፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው በጾም በመጽናታቸው እና ከኃጢአት ራሳቸውን በመጠበቃቸው ባገኙት ኃይለ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ስለዚህ ወጣቶች (የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች) ስንጾም በትምህርታችን ልንደክም እንደምንችል እያሰብን እግዚአብሔር ከሚሰጠን ኃይል እና ጥበብ እንዳንርቅ ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡

ክርስቲያን መንፈሳዊ ተግባራትን በተመቸው ቀን ብቻ የሚተገብር አይደለም በጊዜውም ያለጊዜውም ጸንቶ የሚገኝ ነው እንጂ፡፡ ጾም ሌሎችን ምግባራት (ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት…) ለመፈጸም ፍጹም ኃይልን የምትሠጥ በጎ ተግባር ናት፡፡ የመንፈሳውያን ኃይል የሆኑትን ትዕግሥትን፣ ቸርነትን፣ በጎነትን፣ ራስን መግዛትን … ወዘተ ገንዘብ ለማድረግ ጾም ዋና መሣሪያችን ነው እና ገንዘብ እናድርገው፡፡

፪. ተጋድሎን መፈጸሚያ ነው

በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምንጋደለው ከመንፈሳውያን የክፋት ሠራዊት ጋር እንደሆነ እንዲህ በማለት ተነግሮናል “መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።” (ኤፌ. ፮፥፲፪)፡፡ ለመጋደል የተዘጋጀ ሰው ደግሞ መሣሪያ እንደሚያስፈልገው  ይታወቃል ስለዚህ ጾም ከሁሉ ቀድሞ የሚገኝ ተጋድሎ የመፈጸሚያ መሣሪያ ነው፡፡ በቀንና በሌሊት ከቤተ መቅደስ ሳይለዩ እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ያገለገሉ ቅዱሳን የክፋት ሠራዊትን ድል የማድረግ ኃይልን ተጎናጽፈዋል፡፡ ልባችን በጸጋ እንጂ በምግብ እንዳይጸና ሐዋርያው አስጠንቅቆናል፤ ምግብን አብዝቶ በመብላት እና ለምግብ በማድላት የተጎዳ እንጂ የተጠቀመ እንደሌለ አስተምሮናልና (ዕብ. ፲፫፥፱)፡፡

የተወደዳችሁ ተማሪዎች ተድላና ደስታን በመፈለግ መንግሥተ እግዚአብሔር አትወረስም፡፡ እስኪ ሊቀ ነቢያት ሙሴን እንመልከት ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከክርስቶስ ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መራብን መረጠ፡፡ በዚህ ምክንያት ከሞቀ መኖሪያ ከቤተ መንግሥት ለስደት ተዳረገ፤ ተራበም፤ ተጠማም የሚያገኘውን ዋጋ በዚያ ዘመን ሆኖ ተመልክቷልና (ዕብ. ፲፩፥፳፬-፳፭)፡፡ ይህን በማድረጉ ተጎዳ ወይስ ተጠቀመ? በጣም ተጠቀመ እንጂ የተጎዳው አንዳች አልነበረም፡፡ ሙሴ ለዐርባ ቀናት ከምግብ በመከልከል ከእግዚአብሔር ጋር በመነጋገር ሕግጋትን ታቦትን ከአምላከ ቅዱሳን መቀበል የቻለው በጾም በመጋደሉ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ሰማይን እስከ መለጎም የደረሰ ሥልጣንን ማግኘት የቻለው ዐርባ ቀን እና ሌሊት ለመጾም ይከብድብኛል ሰውነቴ ይከሳል ሳይል ሳይፈራ በጾም በጸሎት በመቆሙ ከክፉዎች ጋር ባለመተባበሩ ነው፡፡ ስለዚህ በረጅሙ የክርስትና ጉዙአችን ውስጥ ጾም በጣም ወሳኝ ነገር መሆኑን ማሰብ እንደሚገባ ልንጋደል ይገባል፡፡ የሥጋችን ፈቃድ ለመግዛት በምናደርገው ተጋድሎ ውስጥ ጾም ጉልህ ሚና አለው፡፡ ጾም የነፍስን ቁስል ትፈውሳለች፤ የሥጋንም ፈቃድ ወይም ፍላጎት ዝም ጸጥ ታሰኛለች እና ለተጋድሎ ጠቃሚ መሣሪያ ናት፡፡

፫. እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመኖር

የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰው ሕያው ሆኖ እንዲኖር ነው፡፡ ማንም በሞት እንዲጠፋ ከገነት ከመንግሥተ ሰማይ እንዲጎድል አይፈልግም፡፡ የሰው ትልቁ ተስፋ መንግሥተ እግዚአብሔርን ወርሶ ዘለዓለማዊ መሆን ነው፡፡ የሕይወት መውጫው ልባችን እንደሆነ መጽሐፍ ይነግረናል “አጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና።” (ምሳ. ፬፥፳፫) አዳም አባታችን አትብላ የምትለውን ሕግ በመሻሩ የሥጋ ፈቃዱን በመፈጸም ከፈቃደ እግዚአብሔር ርቆ በእግረ ሞት ተረግጧል፤ እኛም ከዚህ ሕግ ፈቀቅ ብንል የአዳም ዕጣ ሊገጥመን እንደሚችል ጥርጥር የለውም፡፡ ታዲያ ፈቃደ እግዚአብሔር እየፈጸምን ለመኖር ምን ያስፈልገናል? ካልን ራስን መግዛት የምታስችለውን ጾምን ገንዘብ ማድረግ ነው፡፡ (ኢዩ. ፪፥፲፪) በፍጹም ልብ በመጾም ወደ እርሱ እንድንመለስ መማጸኑ እግዚአብሔር የሚወዳት ጾም ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም የሚያስችል ትልቅ ኃይል እንዳላት ያመለክታል፡፡ ጾም በሰው ጥበብ የተጀመረች ሕግ አይደለችም ምን እንደምትጠቅም የሚያውቅ አምላክ ፈቃዱን እንድንፈጽምባት የሠራት ሕግ ናት እንጂ፡፡

በመጀመሪያ ከመጾማችን በፊት ጾም አድካሚ እና ጎጂ ሕግ ነው ብለን ከመሳት ራሳችንን ልንጠብቅ ይገባል፡፡ ይህ ሕግ የፍቅር ሕግ ነው፤ ከአምላካችን ጋር ኅብረት የምናደርግበት የምሕረት ዓይኑ እንድትመለከተን የምታደርግ ሕግ ስለሆነች በጾም ወደ ፈጣሪ መመለስን እንደ መጎዳት ማሰብ ፈጽሞ ስህተትን ያስከትላልና እንጠንቀቅ፡፡ ፈተና እየተፈተንም ቢሆን እያጠናን ልወድቅ እችላለሁ በሚል ፍርሃት አምላክን ከማሳዘን ከመንግሥቱ ከመጉደል መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡

በአጠቃላይ የክርስትና ዋና ዓላማ በእንግድነት በዚህ ዓለም ባለንበት ዘመን ከፈቃደ ሥጋ መራቅ፤ ነፍስና ሥጋን ማንጻትና የእግዚአብሔር ማደሪያ ማድረግ ነው። ይህ ደግሞ በብዙ ድካምና ተጋድሎ የሚሳካ ነው። በመጽሐፍ “. . . ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል።” (ሐዋ. ፲፬፥፳፪) እንደተባለ መንገዱ የተደላደለ ሳይሆን ብዙ ተጋድሎ የሚያስፈልገው መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል። ገዢዋ የሥጋ ፈቃድ የሆነባት ሰውነት ሞት ያገኛታል “በገዛ ሥጋው የሚዘራ ከሥጋ መበስበስን ያጭዳልና፥ በመንፈስ ግን የሚዘራው ከመንፈስ የዘለዓለምን ሕይወት ያጭዳል።” (ገላ. ፮፥፰) እንዲል ሥጋን በጾም ለነፍስ ማስገዛት ሕይወትን ያስገኛል።

“እንደ ሥጋ ፈቃድ ብትኖሩ ትሞቱ ዘንድ አላችሁና፤ በመንፈስ ግን የሰውነትን ሥራ ብትገድሉ በሕይወት ትኖራላችሁ። በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና። ” (ሮሜ. ፰፥ ፲፫-፲፬) ጾም ፈጽሞ የሥጋ ሥራን ማስወገጃ፣ ተጋድሎን መፈጸሚያ መንገድ ነው።  “መብል ለሆድ ነው፥ ሆድም ለመብል ነው፤ እግዚአብሔር ግን ይህንም ያንም ያጠፋቸዋል። ሥጋ ግን ለጌታ ነው እንጂ ለዝሙት አይደለም፤ ጌታም ለሥጋ ነው” (፩ኛቆሮ. ፮፥፲፫)። ሥጋዊ መብልን በመብላት የሚሠራ ጽድቅ የለም፤ ይልቁንም ብዙ ምግብ ለዝሙት፣ ለትዕቢት የሚያጋልጥ በመሆኑ በጾም ሰውነታችንን ከትዕቢት እንዲሁም ከዝሙት እንጠብቅ። ይህንን ካደረግን ከሆድ ጋር ከመጥፋት ራሳችንን እንታደጋለን። መንፈሳዊ ፍሬን ለማፍራት የምትቀድም ምግባር ጾም ናት ስለዚህ አጥብቀን እንፈልጋት እንያዛትም። “የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችምና።” (ሮሜ. ፲፬፥፲፯) በጾም የምናገኛት ተስፋችን ምን እንደምትመስል በታወቀ ጊዜ ከምግብና ከክፋት በመራቅ የምንገባባት መሆኗንስ ተረዳን? ሰው ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ የሚያስፈልገው ጾም እንጂ ምግብ አይደለም “መብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም፤ ባንበላም ምንም አይጎድለንም ብንበላም ምንም አይተርፈንም።” (፩ኛቆሮ. ፰፥፰) እንደተባለ። የምግብ ኃይል ለሥጋ ነው የጾም ኃይሏ ግን ለነፍስ ነው “የክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑት ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ።” (ገላ. ፭፥፳) የተባለውን እናስተውል።

ይቆየን

ጾመ ነነዌ

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ ታሪኮች አንዱ ትንቢተ ዮናስ ሲሆን ሰብዓ ነነዌ ኃጢአት በመሥራት እግዚአብሔርን መበደላቸውና ማሳዘናቸውን፤ በዚህም ምክንያት እግዚአብሔር መቅሰፍቱን በሕዝቡና በሀገሪቱ ላይ ከማውረዱ በፊት ንስሓ ይገቡ ዘንድ ነቢዩ ዮናስን እንደላከው እንመለከታለን፡፡ዮናስ ማለት ርግብ ማለት ነው፡፡ ርግብ የዋህ፣ ኃዳጌ በቀል እንደሆነች ሁሉ ዮናስ በሌሎች ላይ ተንኮል የማይሠራ ነውና፡፡ ትንቢተ ዮናስ የተጻፈው ከአሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት መካከል አንዱ በሆነው ነቢየ እግዚአብሔር ዮናስ ሲሆን ዘመኑም ከክርስቶስ ልደት በፊት በስምንተኛ ክፍለ ዘመን እንደሆነ ይታመናል፡፡ ተንቢተ ዮናስ አራት ምዕራፎችንና አርባ ስምንት ቁጥሮችን ያቀፈ ነው፡፡ በመጽሐፉ ውስጥ ከተጠቀሱት ቦታዎች መካከልም ኢዮጴ፣ ተርሴስና ነነዌ ይገኙበታል፡፡

የነነዌ ሰዎች በደል እጅግ የከፋ ነበርና እግዚአብሔር ዮናስን አሥነስቶ “ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፡ ክፋታቸውም ጩኸት ወደ ፊቴ ወጥቶአልና ለእነርሱ ስበክ፡፡” በማለት ሕዝቡ ወደ ንስሓ ይመለስ ዘንድ እንዲሰብክ አዘዘው፡፡ ነቢዩ ዮናስ ግን የሕዝቡ ልብ ደንድኗልና እኔ ይህን እንዴት ማድረግ ይቻለኛል በሚል የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ጥሶ ከነነዌ ወደ ተርሴስ ለመኮብለል ወደ ኢዮጴ አመራ፤ በዚያም ወደ ተርሴስ የምትሄድ መርከብ አገኝቶ ወደ ተርሴስ ተሳፈረ፡፡ ነገር ግን እንዳሰበው ወደ ተርሴስ መሄድ አልቻለም፡፡

እግዚአብሔርም በባሕሩ ላይ ታላቅ ነፋስን አነፈሰ፤ ታላቅም ማዕበል በመነሣቱ መርከቧ ልትሰበር ደረሰች፡፡ በውስጡ የተሳፈሩት መንገደኛም ታላቅ ፍርሃትን ፈሩ፡፡ በመርከቢቱ ውስጥ የነበሩትን እቃዎች ሁሉ ወደ ባሕሩ ቢጥሉም መርከቢቱ ከመናወጥ አልዳነችም፡፡ ዮናስ ግን በታችኛው የመርከቢቱ ክፍል እንቅልፉን ተኝቶ አገኙት፡፡ የመርከቢቱም አለቃ ወደ ዮናስ መጥቶ “ምነው ተኝተሃል? እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ያድነን ዘንድ ተነሥተህ አምላክህን ጥራ” አለው፡፡ እርስ በርሳቸውም “ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት መጣብን?” በማለት ዕጣ ተጣጣሉ፡፡ ዕጣውም በዮናስ ላይ ወደቀ፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ዮናስም ይህ በእርሱ ምክንያት እንደደረሰባቸው በመረዳቱ “ይህ ታላቅ ማዕበል በእኔ ምክንያት እንደ አገኛችሁ ዐውቃለሁና አንሥታችሁ ወደ ባሕሩ ጣሉኝ፤ ባሕሩም ጸጥ ይልላችኋል” አላቸው፡፡ ዮናስንም ወስደው ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ ማዕበሉም ጸጥ አለ፡፡ እግዚአብሔር በባሕሩ ውስጥ ዮናስን ይውጠው ዘንድ ዓሣ አንበሪውን አዘዘ፡፡ ዮናስም በዓሣ አንበሪው ሆድ ውስጥ ሳለ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ የልቡን ቅንነትና ንጽሕና እግዚአብሔር ያውቃልና ለነቢዩ ዮናስ አዘነለት በዓሣ አንበሪው ሆድ ውስጥ ለሦስት ቀንና ሌሊት አድሮ በእግዚአብሔር ቸርነት ዓሣ አንበሪው ዮናስን በየብስ ላይ ተፋው፡፡

የእግዚአብሔርም ቃል ለሁለተኛ ጊዜ ወደ ዮናስ መጣ፡- “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የነገርሁህን የመጀመሪያውን ስብከት ስበክላት” አለው፡፡ ዮናስም ወደ ነነነዌ ሄዶ እየጮኸ “በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለበጣለች” አለ፡፡ የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾምም ዐዋጅ ነገሩ፡፡ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፡፡ ንጉሡም ከዙፋኑ ተነሥቶ ማቅ ለብሶ በራሱ ላይ አመድ ነስንሶ ዐዋጅ አስነገረ፡፡ እንዲህም አለ “ሰዎችና እንስሶች፣ ላሞችና በጎች አንዳች አይቅመሱ፤ አይሰማሩም ውኃም አይጠጡ፣ ከከፉ መንገዳቸውም ይመለሱ” በማለት አዘዘ፤ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ ከተናገረው ክፉ ነገር ተመለሰ፤ አላደረገውምም፡፡

ነቢዩ ዮናስ ግን እግዚአብሔር ከቁጣው በመመለሱና ሕዝቡንም ይቅር በማለቱ እጅግ ተበሳጨ፡፡ “አቤቱ በሀገሬ ሳለሁ የተናገርሁት ይህ አልነበረምን? አንተ ቸርና ይቅር ባይ፣ ታጋሽም፣ ምሕረትህም የበዛ ከክፉው ነገርም የምትመለስ አምላክ እንደሆን ዐውቄ ነበርና ስለዚህ ወደ ተርሴስ ለመኮብለል ፈጥኜ ነበር፡፡ አሁንም አቤቱ ከሕይወት ሞት ይሻለኛልና እባክህን ነፍሴን ከእኔ ውሰድ” በማለት ከእግዚአብሔር ጋር ተሟገተ፡፡ ዮናስም ከከተማይቱ ወጥቶ አንዲት ዛፍ (ድንኳን) ከጥላው በታች ተቀመጠ፡፡

እግዚአብሔር ዮናስን ከፀሐዩ ግለት ይከላከልለት ዘንድ ቅልን አዘዘ፤ ከራሱ በላይም ጥላ እንድትሆነው ከፍ ከፍ አደረጋት፡፡ ዮናስም ስለ ቅሊቱ እጅግ ተደሰተ፡፡ በነጋም ጊዜ እግዚአብሔር ትልን አዝዞ ቅሊቱን መታቻት፤ ቅሊቱም ደረቀች፡፡ እግዚአብሔርም የምሥራቅን ነፋስ በማዘዝ ዮናስን ፀሐዩ ራሱን መታው፡፡ “በሞትኩ ይሻለኝ ነበር” ብሎም ተበሳጨ፡፡ እግዚአብሔር ግን ዮናስን ዝም አላላውም “አንተ ትበቅል ዘንድ ላልደከምህባት፣ ላላሳደግሃትም በአንድ ሌለት ለበቀለች፣ በአንድ ሌሊትም ለደረቀችው ቅል አዝነሃል፡፡ እኔስ ቀኛቸውንናግራቸውን የማይለዩ ከመቶ ሃያ ሺህ የሚበልጡ ሰዎችና እንስሶች ላሉባት ለታላቂቱ ከተማ ለነነዌ አላዝንም?” አለው፡፡

ነቢዩ ዮናስ ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ወጥቶ በራሱ መንገድ በመሰለው የተጓዘበት መንገድ አላዋጣውም፡፡ ከእግዚአብሔርም ትእዛዝና ፈቃድ መውጣት ቅጣቱ የከፋ መሆኑን ከነቢዩ ዮናስ ታሪክ መረዳት እንችላለን፡፡ የነነዌ ሰዎች ግን በአንድ ዮናስ ስብከት ከበደላቸው ተመልሰው፣ ማቅ ለብሰው፣ አመድ ነስንሰው ከመሬት ወድቀው እግዚአብሔር ምሕረቱን ይልክላቸው ዘንድ በመለመናቸው እግዚአብሔር አዘነላቸው፣ የምሕረት ፊቱንም መልሶ ይቅር አላቸው፡፡ ንስሓ ምን ያህል ዋጋ እንዳለውም በዚህ እንረዳለን፡፡ እኛም ለእግዚአብሔር በመታዘዝ በንስሓ ተመልሰን የስሙ ቀዳሾች የመንግሥቱ ወራሾች እንሆን ዘንድ ምግባር ከሃይማኖት አስማምተን ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶ ልናፈራ ይገባል፡፡ ሰብዓ ነነዌን ከጥፋት የታደገ አምላካችን ሀገራችንና ሕዝቦችዋን  ከጥፋት ይጠበቅልን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አዲሱን የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት የሙከራ ትግበራ ለሚያስፈጽሙ ሠልጣኞች የተሰጠው ሥልጠና ተጠናቀቀ

ማኅበረ ቅዱሳን ለሦስተኛ ጊዜ የተገመገመውንና ለሁለተኛ ጊዜ የተከለሰውን አዲሱን የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት ለሚያስፈጽሙ መምህራንና አስተባባሪዎች ከጥር ፴ እስከ የካቲት ፪ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ለሁለት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የነበረው የአሠልጣኞች ሥልጠና ተጠናቀቀ፡፡

ሥልጠናው ከአቀባበል ጀምሮ ለሁለት ተከታታይ ቀናት ከቀድሞው ሥርዓተ ትምህርት ግምገማ አንስቶ የሥርዓተ ትምህርቱን የክለሳ ኀላፊነት ወስደው ሲያዘጋጁ በነበሩ ከፍተኛ የትምህርት ዝግጅትና ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች የተሰጠ ሥልጠና ነው፡፡

ሥልጠናው በዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል “የሥልጠናው ዓላማ እና ሠልጣኞች ተሸክመው ሊሄዱ የሚገባቸውን ተልእኮ በተመለከተ፣ የሙከራ ትግበራ ምን? ለምን/ እንዴት/፣ ክፍል አንድ የሥርዓተ ትምህርቱ መሠረታዊ ጉዳዮች፣ የነባሩ ሥርዓተ ትምህርት ግምገማ መሠረታዊ ግኝቶች፣ የሥርዓተ ትምህርቱ ተለማጭነት አተገባበር፣ ዝቅተኛ የመማር ብቃት፣ የተመረጡ የትምህርት ዓይነቶችን እንደማሣያ” በተሰኙ ርእሰ ጉዳዮች ለአንድ ቀን ሙሉ ሥልጠናውን ሰጥተዋል፡፡

የካቲት ፪ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም በቀጠለው የአሠልጣኞች ሥልጠናም በዶ/ር ወርቁ ደጀኔ “አሳታፊ የመማር ማስተማር ዘዴ፣ ጠማሪዎች አያያዝድጋፍ” እንዲሁም በዶ/ር ቴዎድሮስ ሀብቴ “በሥርዓተ ትምህርቱ ትግበራ ከመምህራን የሚጠበቁ ክሂሎቶች፣ የምዘናና ግምገማ ሥርዓት” በሚሉ ርእሰ ጉዳዮች ሰፊ ትንታኔ የቀረበ ሲሆን ከተሳታፊዎች ለሚቀርቡ ጥያቄዎችም በምሁራኑ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

ሥልጠናውን ከወሰዱት መምህራንና አስተባባሪዎች መካከል ከአዳማ ማእከል ተወክለው የመጡት ዲ/ን መብራቱ ስንታየሁ ስለ ሥልጠናው ሲገልጹ፡- “በሥልጠናው ስለ አዲሱ ሥርዓተ ትምህርት ሰፊ ግንዛቤ እንዲኖረኝ፣ ነባሩ ሥርዓተ ትምህርት በምን ምክንያት መከለስ እንዳስፈለገውና በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርትም የተካተቱት መሠረታዊ ጉዳዮች እንድረዳ አስችሎኛል፡፡ ወደ ማእከል ተመልሼም ባገኘሁት ሥልጠና መሠረት ሥርዓተ ትምህርቱ በግቢ ጉባኤያት ላይ እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባን ለሚመለከታቸው አካላት በማስረዳት ተግባራዊ እናደርግ ዘንድ በቁርጠኝነት እናገለግላለን” በማለት ገልጸዋል፡፡

ከወልቂጤ ማእከል የመጡት ዲ/ን አበበ ስሜ ስለ ሥልጠናውና ከሥልጠናው የተረዱትን ሲገልጹ “ባለፉት ሦስት ተከታታይ ቀናት የወሰድነው ሥልጠና አዲሱ ሥርዓተ ትምህርትን በተመለከተ በበቂ ሁኔታ ግንዛቤው እንዲኖረኝ፣ የተካተቱት አዳዲስ ነጥቦችንም እንድረዳ አስችልኛል፡፡ የትምህርት አሰጣጡንም ሕይወት ተኮር እንዲሆን፣ ተማሪዎች መንፈሳዊ ሕይወትን እንዲለማመዱና በዚያም ጸንተው እንዲኖሩ የሚያግዝ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ከማእከል ወንድሞችና እኅቶች ጋር በመሆን ሥርዓተ ትምህርቱ ወደ መሬት በማውረድ ውጤታማ ሥራ ለመሥራት ጥረት እናደርጋለን” በማለት ሥልጠናው ኃላፊነትን በአገባቡ መወጣት እንዲችሉ ግንዛቤ እንደፈጠራላቸው አስረድተዋል፡፡   

ከሥልጠናው በኋላም በተከናወነ የመዝጊያ ሥነ ሥርዓት የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ኀላፊ አቶ አበበ በዳዳ “ከሥርዓተ ትምህርቱ ግምገማ ጀምሮ የክለሳውን ኀላፊነት በመውሰድ ሲያዘጋጁ የነበሩት ምሁራን አብረውን አሉ፡፡ ከአሁን በኋላም በርካታ ሥራዎች ይጠብቀናል፡፡ የመጻሕፍት ዝግጅት፣ የድኅረ ምረቃ እና የውጪ ማእከላት ግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት ዝግጅት፣ መጻሕፍቱ በተለያዩ ቋንቋዎች የሚተረጎሙ በመሆኑ እነዚህ ምሁራን አብረውን ይቆያሉ፡፡ በዚህም መሠረት አገልግሎት ወስዶ ለፍጻሜ በማብቃትና ውጤታማ ሥራ የሚሠራውን ደግሞ እናመሰግናለን ማለትን መልመድ አለብን” በማለት በሥርዓተ ትምህርቱ ግምገማና ክለሳ ላይ ለተሳተፉት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት መ/ር ዋሲሁን በላይ ባስተላለፉት መልእክትም “ዓላማችንን ለማሳካት የተማረ የሰው ኃይል ስናፈራ ብቻ ነው፡፡ ይህን የሰው ኃይል ማፍራት የሚቻለው ደግሞ በተዘጋጀ ሥርዓተ ትምህርት ነው፡፡ ሰው ላለመው ዓላማ የሚበቃው በዚህ መንገድ ሲያልፍ ብቻ ነው፡፡ በሥርዓተ ትምህርት ያላለፈ ሰው ተጎጂ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ሠልጣኞች ወደየማእከሎቻችሁ ስትሄዱ ለማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ፣ ለመምህራን፣ ለማኅበራችን አባላት፣ ተባበሪ አካላት (ሰበካ ጉባኤ፣ ሰ/ት/ቤቶች) ማኅበረ ቅዱሳን ሥርዓተ ትምህርቱን እንደለወጠ (እንደከለሰ) በሚገባ የማስረዳትና የማሳወቅ ኃላፊነት አለባችሁ፡፡ ከእናንተ ውጪ ለዚህ ሥርዓተ ትምህርት መተግበር ጥብቅና የሚቆም ስለሌለ አብዝታችሁ መትጋት ይጠበቅባችኋል” ብለዋል፡፡

በሥርዓተ ትምህርት ግምገማና ክለሳ ለተሳተፉት ከፍተኛ ባለሙያዎችና መምህራንም “ላለፉት ዓመታት የከፈላችሁት ኃላፊነት የተሞላበት አገልግሎት በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን” በማለት ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡      

የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሄኖክ “ሁሉም ነገር በሥርዓት ይሁን” እንዲል ትምህርትም በሥርዓት ካልሆነ ውጤታማ መሆን አይቻልም፡፡ ትምህርት ሥርዓተ ትምህርት ተበጅቶለት ተለክቶና ተቀምሞ ሲቀርብ ውጤታማ ይሆናል፡፡ ስለዚህ ይህን ያህል ጊዜ ሲሊለፋበት የቆየው ውጤታማ እንዲሆን ነው፡፡ ለውጤታማነቱ ደግሞ የሙከራ ትግበራ ለማድረግ እናንተ ሠልጣኞች ተመርጣችኋል፡፡ ይህንንም ሥርዓተ ትምህርት ይዛችሁ ከሥር ላሉት መምህራን፣ አባላትና ምእመናን ተደራሽ ለማድረግ ትልቅ ኃላፊነት የተጣለባችሁ መሆኑን ተረድታችሁ በትጋት ማስፈጸም ይጠበቅባችኋል” ብለዋል፡፡

በመጨረሻም ሥርዓተ ትምህርቱን በመገምገምና በመከለስ ለተሳተፉ ከፍተኛ ባለሙያዎችና መምህራን የማስታወሻ ስጦታ የተበረከተላቸው ሲሆን ለሠልጣኞቹም የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል፡፡

አዲሱን ሥርዓተ ትምህርት የሙከራ ትግበራ ለሚያስፈጽሙ አገልጋዮች ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል

ማኅበረ ቅዱሳን ለሁለተኛ ጊዜ የተከለሰውንና ለሦስተኛ ጊዜ የተዘጋጀውን ሥርዓተ ትምህርት ለመተግበር ከተመረጡ ማእከላት ለተውጣጡ መምህራንና አስተባባሪዎች የአሠልጣኞች ሥልጠና ከጥር ፴ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ተከታታይ ቀናት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

ማኀበረ ቅዱሳን የመጀመሪያውን የሥርዓተ ትምህርት ክለሳ በ፳፻፮ ዓ.ም አድርጎ የነበረ ሲሆን ለአሥር ዓመታት አገልግሎት ላይ በማዋል ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትህምርት በተከታታይ ትምህርት (course) ሲያስተምር ቆይቷል፡፡

በአሁኑ ወቅት ቀድሞ የነበረውን ሥርዓተ ትምህርት መከለስ ያስፈለገበት ምክንያት የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ኀላፊ የሆኑት አቶ አበበ በዳዳ ሲገልጹ፡- “ላለፉት አሥር ዓመታት ሲተገበር የነበረው ሥርዓተ ትምህርት በተደረገው የግምገማ ውጤት መሠረት አንዳንድ ጉድለቶች በመታየታቸው ነው፡፡” ብለዋል፡፡

እንደ ምሳሌም ሲጠቅሱ “በሥርዓተ ትምህርቱ ላይ የታዩ ጉድለቶች፣ በማኅበረ ቅዱሳን ተቋማዊ ለውጥ ትግበራ ላይ ስለ ግቢ ጉባኤያት የተካተቱት ሐሳቦች፣ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተመርቀው ሲወጡም ዘመኑን የዋጁ፣ ምሉእ የሆኑና ቤተ ክርስቲያንና ሀገርን በተለያዩ ዘርፎች በሙያቸው እንዲያገለግሉ ለማስቻል፣

የሰ/ት/ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት በ፳፻፲፩ ዓ. ም ለአገልግሎት መዋልና ከአንዳንዶቹ ጋር ተመሳሳይ መሆናቸው፣ በድጋሚ ከማስተማር ከዚያ የቀጠለው ላይ ትኩረት ማድረግ ስላስፈለገ፣

የትምህርት ሚኒስቴር ፍኖተ ካርታ/ፖሊሲ/ መቀየር (ከሦሰት ዓመት ወደ አራት ዓመት ከፍ መደረጉ) ክለሳ ለመደረጉ እንደ ምክንያት ጠቅሰዋል፡፡

የአሠልጣኞች ሥልጠናውን የሚወስዱት መምህራንና አስተባባሪዎች የተመረጡት በወጣላቸው መስፈርት መሠረት ደረጃ አንድና በከፊል ደግሞ ደረጃ ሁለት ካሟሉ ግቢ ጉባኤያት ውስጥ ነው፡፡ ሥልጠናውን እየሰጡ የሚገኙት በሥርዓተ ትምህርት ዝግጅት ከፍተኛ ልምድ ባላቸውና በነባሩ ሥርዓተ ትምህርቱ ላይ የግምገማ ሥራ በመሥራት ክለሳውን በማዘጋጀት ሰፊ ድርሻ ባላቸው ምሁራን አገልጋዮች ነው፡፡

በዛሬው ውሎም የሥልጠናው ዓላማና ሠልጣኞች ይዘው ሊሄዱ የሚገባቸውን ተልእኮ፣ የሙከራ ትግበራ ምን? ለምን? እንዴት? ክፍል አንድ የሥርዓተ ትምህርቱ መሠረታዊ ጉዳዮች፣ የነባሩ ሥርዓተ ትምህርት ግምገማ መሠረታዊ ግኝቶች፣ የሥርዓተ ትምህርቱ አደረጃጀትና አተገባበር ዕሳቤዎች በተለመከተ በባለሙያዎቹ ሰፊ ትንተና ተሠጥቷል፡፡  

በሥልጠናው ከ፲፪ ማእከላት የተውጣጡ መምህራንና አስተባባሪዎች ሲሆኑ ሙሉ ለሙሉ የተከለሰውን ሥርዓተ ትምህርት ከመተግበሩ በፊት በእነዚህ በተመረጡ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት የሙከራ ትግበራ የሚከናወን ይሆናል፡፡ ሥልጠናው በነገው ዕለትም ቀጥሎ ይውላል፡፡    

“ጌታ እግዚአብሔር ተገለጠልን” (መዝ. ፻፲፯፥፳፮)

በመ/ር ብዙወርቅ አበበ (ከአምቦ ማእከል)

አስተርእዮ ማለት መገለጥ ፣ መታየት ማለት ነው፡፡ አስተርእዮ የሚለው ቃል በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ “ኤጲፋኒ” ይባላል፤ ይህም ከላይ መታየት፣ መገለጥ የሚለውን ለየት አድርጎ ያስረዳል፡፡

በክርስትና ሃማኖት ደግሞ አስተርእዮ ወይም ኤጲፋንያ የአምላክን መገለጥ፣ መታየት የሚያመለክት ነው፡፡ ከልደተ ክርስቶስ ዋዜማ ጀምሮ እስከ ዐቢይ ጾም ድረስ ባሉት ሳምንታትና ቀናት “ተወልደ (ተወለደ)፣ አንሶሰወ (ተመላለሰ)፣ አስተርአየ (ታየ)፥ ተጠመቀ፣ …” የሚሉት ቃላት በብዛት ይነገራሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያንም እነዚህን ቀናት ዘመነ ጥምቀት ወአስተርእዮ ብላ ታከብራለች፤ በእነዚህ ዕለታትና ሳምንታት በቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው መዝሙርም ሆነ የሚነበበው ንባብ ይህንኑ የጌታን መገለጥ የሚናገር፤ ስለ አምላክ ሰው መሆን፤ ስለ ሰማያዊ ሙሽራ መምጣት፣ መታየትና መገለጥ፣ በዚህ ምድር ተመላልሶ ማስተማር የሚያወሳ ነው፡፡

የረቂቅ አምላክን በሥጋ መገለጥ በዓይነ ትንቢት የተመለከተ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት “እግዚአብሔር እግዚእ አስርአየ ለነ፤ ጌታ እግዚአብሔር ተገለጠልን” ሲል ተናግሯል፡፡
በዚህ ገጸ ንባብ ውስጥ የምንመለከተው እግዚአብሔር በየጊዜው በሕልም፣ በራእይ ወይም በልዩ ልዩ ተምሳሌት የሚደረገውን መገለጥ ሳይሆን ዓመተ ኩነኔን ለማሳለፍ ዓመት ምሕረትን ለማወጅ  በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ ከመካከላችን የተገኘውን የመድኃኔዓለም መገለጥ  ነው፡፡

በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔርን በምሳሌ እንጂ ፊቱን ያየው አልነበረም፤ ሙሴ ከባለሟልነቱ የተነሣ “በባሕርይ ሆነህ ልይህ” ቢለው “ፊቴን አይቶ ለአንዲት ደቂቃ እንኳን በሕይወት ለመቆየት የሚችል የለም” ብሎታል፡፡ (ዘፀ. 3፴፭፥፲፯‐፳፭) ኋላም ወንጌላዊው ዮሐንስ “እግዚአብሔርን በባሕርይው ያየው የለም” ብሏል፡፡ (ዮሐ. ፩፥፲፰)

አዳምና ሔዋን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በማፍረሳቸው በመከራ አዘቅት ውስጥ ወድቀው ሲሠቃዩ ወደዚህ ዓለም መጥቶ ሰው ሆኖ ከድንግል ማርያም ተወልዶ፣ ተጠምቆ፣ እየተመላለሰ አስተምሮ፣ ተሰቅሎ፣ ሞቶ፣ ተነሥቶ፣ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ እንደሚያድናቸው ተስፋ ሰጣቸው፡፡ የሰጣቸው ተስፋ ዕለቱን አልተፈጸመም፤ በትንቢት እየተነገረ፣ በሱባኤ እየተቆጠረ፣ በምሳሌም እየተመሰለ ብዙ ዘመን ኑሯል፡፡

ስለ ክርስቶስ በሥጋ መገለጥ ነቢያት ብዙ ትንቢት ተንብየዋል፤ ሱባኤም ቆጥረዋል፤ ምሳሌም እየመሰሉ ተናግረዋል፤ የተነገረው ትንቢት ሲፈጸም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ በአጭር ቁመት፤ በጠባብ ደረት ተገለጠ፤ ከተወለደም በኋላ አምላክ ነኝ ብሎ ዕለቱን አላደገም፤ እንደ ሕፃናት ቀስ በቀስ አደገ እንጂ፡፡

የዕብራውያንንም ሕግና ሥርዓት አላፋለሰም፤ በተወለደ በስምንተኛው ቀን ወደ ቤተ ግዝረት ገብቶ የግዝረት ሥርዓት ተፈጽሞለታል፤ ስሙም ኢየሱስ ተብሎ ተሰይሟል፡፡ በዐርባኛው ቀን ደግሞ እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምና ቅዱስ ዮሴፍ ዕጕለ ርግብ ዘውገማ ማዕነቅ ይዘው ወደ ቤተ እግዚአብሔር ወስደውታል፤ በዓመትም ሦስት ጊዜያት ወደ ቤተ መቅደስ ይወስዱት ነበር፡፡

ይህ አስተርእዮ በዘመነ ብሉይ ከነበረው መገለጥ በመልክም በጠባይም ይለያል፤ ያኛው በሕልም፣ በራእይ፣ በምሳሌ ነበር፤ አሁን ግን ራሱ የሰው ልጅ ለማዳን ተገለጠ፥ የፊተኛው ለተወሰኑ ሰዎች ነበር፤ አሁን ግን ለመላው ዓለም ሆነ፤ የፊተኛው በሩቅ ነበር፤ አሁን ግን በቅርብ የእኛን ሥጋና ነፍስ ተዋሕዶ ታየ፡፡ በዚህ አስተርእዮ በሰማይ ያለው የእግዚአብሔር መቅደስ ተከፈተ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ተተከለ፤ ማለትም በሰዎች መካከል ተገኘ፤ ሰዎች የእግዚአብሔር ባለሟሎች ሆኑ፤ በእጃቸው ዳሰሱት፤ በዓይናቸውም አዩት፤ ሲያስተምር ሰሙት፤ አብረውት ተመገቡ፡፡  

ሰው የእግዚአብሔርን ክብር አየ፤ በዚህ አስተርእዮ በምሥጢረ ሥጋዌ ምሥጢረ ሥላሴንም ተማርን፤ አየን፤ በዮርዳኖስና በደብረ ታቦር አብ ስለ ልጁ የተናገረውን የምስክርነት ቃል ሰማን፤ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል መጥቶ በራሱ ላይ ሲቀመጥ ተመለከትን፤ በዚህም የአካል፣ የስም፣ የግብር ሦስትነታቸውን የፈቃድ፣ የሕልውና አንድነታቸውን ተረዳን፡፡

በመንፈስም በገንዘብም ድሆች ተብለው ተንቀው ለነበሩት እግዚአብሔር በመካከላቸው ተገኘ፤ በዓለማዊ ሥልጣናቸው የሚመኩ ትዕቢተኞች ተዋረዱ፤ ትሑታን ከፍ ከፍ አሉ፤ የፍትሕ ሚዛን የሌላቸው ነገሥታት ተንኮታኩተው ወደቁ፤ የተራቡ በአስተርእዮ በረከት ጠገቡ፤ የተጠሙት ረኩ፤ በኃላፊ ሀብታቸው በመመካት እግዚአብሔርን ንቀው የነበሩ ሀብታሞች ባዶ እጃቸውን ቀሩ፡፡

በዚህ በዘመነ አስተርእዮ ወቅት የሚከበሩ በዓላት ከዋሉበት የአስተርእዮ ዘመን የተነሣ የአስተርእዮ በዓላት ይባላሉ፡፡ የሚነገርባቸውም ቃለ እግዚአብሔር ስለ ጌታ መወለድ፣ በግልጥ መመላለስ፣ መጠመቅ፣ አምላክ ሰው ስለመሆኑ ምሥጢረ ሥላሴ ስለመገለጡ ነው። በተለይም ጥር ፳፩ የእመቤታችን የዕረፍት በዓል አስተርእዮ ማርያም ይባላል። በተለየ አስተርእዮ ማርያም መባሏ ለቃል ርደት፣ ለሥጋ ዕርገት ምክንያት ናትና ነው፡፡ እንዲሁም ምሥጢረ ሥላሴ በምልዓት የተገለጠው አምላክ ከእሷ ሰው ከሆነ በኋላ ስለሆነ በዓሉ አስተርእዮ ማርያም ይባላል።

አስተርእዮ ማርያም ብለን የምናከብረው በዓል የእመቤታችንን የዕረፍት በዓል ነው። ቅዱስ ዳዊት “ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ሀገረ እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር ማኅፀንሽን ከተማ አድርጎ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን የኖረብሽ ሆይ ስለ አንቺ የተነገረው የተደረገው ነገር ዕፁብ ድንቅ ነው” (መዝ. ፹፮፥፫) እንዳለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ እናት ሆና ማረፏ ይደንቃል። ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ ሞቷ የሚያስደንቅ መሆኑን “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኲሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው ሁሉ የተገባ ነው የማርያም ሞት ግን ሁሉን ያስደንቃል” በማለት ገልጾታል።

ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሞትና ትንሣኤ በነገረ ማርያም አበው እንደሚያስረዱት ዕረፍቷ በጥር ፳፩ እሑድ ነው ። አባቶቻችን በጾመ ፍልሰታ ውዳሴ ማርያም፣ ቅዳሴ ማርያም ሲተረጉሙ የዕረፍቷን ነገር እንዲህ ብለው ይተርካሉ።

የዕረፍቷስ ነገር እንደምን ነው ቢሉ ስድሳ አራት ዓመት በዚህ ዓለም ኖራ ጥር ፳፩ በእሑድ ቀን ጌታ እልፍ አዕላፋት መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ “እናቴ ሆይ! ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍሽ መጣሁ” አላት። “ልጄ ሆይ! ሰማይና ምድር የማይወስኑህ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኔ ተሸክሜ በድንግልና ወልጄህ እሞታለሁን?” አለችው። በሲኦል የሚሠቃዩ ነፍሳትን አሳይቶ “እናቴ ሆይ! ሞትሽ ለእነዚህ ቤዛ (የመዳን ምክንት) ይሆንላቸዋል” አላት። እሊህን ከማርክልኝስ ይሁን አለችው። ቅድስት ሥጋዋን ከቅድስት ነፍሷ ለይቶ በቃለ አቅርንት፣ በዝማሬ መላእክት አሳረጋት። ደቀ መዛሙርቱንም ከያሉበት በደመና ጠቅሶ ካለችበት አድርሶ እመቤታችሁን ሥጋዋን በክብር አሳርፉ አላቸው። ሐዋርያት በአጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘው ሲሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ተነሣ፤ ዐረገ እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ፤ አሁን ደግሞ እሷን ተነሣች፤ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ። ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው። መልአክ መጥቶ በሰይፍ ሁለት እጁን ቀጣው፤ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ። “በድያለሁ ማሪኝ” ብሎ ቢማጸናት እጁ ተመልሶለታል። ከዚህ በኋላ ጌታችን ከዮሐንስ ጋር በደመና ነጥቆ ከገነት አግብቶ ከዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት።

ቅዱስ ዮሐንስን “እንደምን ሆነች?” አሉት ከገነት “ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች” አላቸው፡፡ እነርሱም ቅዱስ ዮሐንስ አይቶ እኛ ሳናይ ብለው በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፤ ሁለት ሱባዔ ሲፈጸምም እሑድ አምጥቶ ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፤ በሦስተኛው ቀን ማክሰኞ ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ተነሥታለች።

በቦታው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፤ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬም ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን” ብሎ ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ፤ ከሐዘኑ የተነሣ ሊወድቅ ወደደ፡፡ እመቤታችንም “አይዞህ አትዘን! እሊያ ትንሣኤዬን፣ ዕርገቴን አላዩም፤ አንተ አይተሃል፤ ተነሣች ዐረገች” ብለህ ንገራቸው ብላ የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው።

ከዚህ በኋላ ቅዱስ ቶማስ ወደ ሐዋርያቱ ሄዶ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው። ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ ልማድህ ነው አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” ብሎ ተቆጥቶ ወደ መቃብሩ ሂዶ ቢከፍተው አጣት፤ ደንግጦ ቆመ፡፡ ሐዋርያው ቶማስም አታምኑኝም ብዬ እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች፤ ዐረገች አላቸው፤ የያዘውንም ሰበን ሰጣቸው፤ ለበረከትም ተካፍለውታል።

በዓመቱ ሐዋርያት ቅዱስ ቶማስ “ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው ጾም ጀመሩ፡፡ በ፲፮ኛው ቀን እመቤታችንን መንበር አድርጎ ቅዱስ ጴጥሮስን ካህን ዘይትራድኦ ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ በዚያው ላይ ቀድሶ አቁርቧቸዋል።

ቤተ ክርስቲያንም ይህንን መሠረት አድርጋ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ መወለዱን (መገለጡን) እንዲሁም የእመቤታችንን ዕረፍት ምክንያት በማድረግ መታሰቢያ በዓሉን ጥር ፳፩ ቀን በየዓመቱ ታከብረዋለች።

ቃና ዘገሊላ

በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ!

እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን!

በመ/ር ቢትወደድ ወርቁ

የልደትና የጥምቀት ዘመን በጽርዕ ቋንቋ ኤጲፋኒ፣ በግእዝ ዘመነ አስተርእዮ፣ በአማርኛ የመገለጥ ዘመን ይባላል። ጥምቀት የሚለው ቃል “አጥመቀ” ከሚለው የግእዝ ቃል/ግሥ የተገኘ ሲሆን በቀጥታ ሲተረጎም በውኃ ውስጥ ገብቶ መውጣት፣ መጠመቅ ማለት ነው። በምሥጢራዊ ትርጉሙ ግን ጥምቀት ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንዱ ሲሆን ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ተወልደን የሥላሴን ልጅነት የምናገኝበት፣ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት፣ ኀጢአታችን የሚደመሰስበትና ድኅነትን የምናገኝበት ዐቢይ ምሥጢር ነው። (ዮሐ. ፫፥፭)

ጥምቀት በምሥጢረ ሥላሴና በምሥጢረ ሥጋዌ አምኖ ለሚቀበለው ሰው ሁሉ ከሥላሴ የጸጋ ልጅነት ለማግኘትና የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የተሰጠ ልዩ ክርስቲያናዊ የሕይወት መንገድ ነው። ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጢባርዮስ ቄሣር በነገሠ በ፲፭ኛው ዓመት፣ በተወለደ በሠላሳ ዓመቱ፣ በዕለተ ማክሰኞ ከሌሊቱ በዐሥር ሰዓት፣ ዮር እና ዳኖስ የተባሉ ወንዞች በሚገናኙበት በተቀደሰው የዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ (ማቴ. ፫፥፲፫-፲፯፣ ማር. ፩፥፱-፲፩፣ ሉቃ. ፫፥፳፩-፳፪፣ ዮሐ. ፩፥፳፱-፴፬) የተጠመቀውም የካህኑ ዘካርያስና የቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ በሆነው፣ ገና የስድስት ወር ፅንስ ሳለ በማኅፀን በሰገደለት፣ በበረሀ ባደገው፣ መንገድ ጠራጊ በተባለው፣ የንስሓን ጥምቀት በዮርዳኖስ ሲያጠምቅ በነበረውና ኋላም በንጉሥ ሄሮድስ ዘመን እውነትን መስክሮ ሰማዕትነትን በተቀበለው በመጥምቀ መለኮት በቅዱስ ዮሐንስ እጅ ነው፡፡ ከውኃ ውስጥ ገብቶ በመውጣትም ተጠመቀ፡፡

ጌታችን የተጠመቀው ሕዝቡ ሁሉ ከተጠመቁ በኋላ ነበር፡፡ ይህም የራሱ የሆነ ምክንያት አለው፡፡ ከሕዝቡ አስቀድሞ ተጠምቆ ቢሆን የኦሪት ጥምቀትን ተጠመቀ እንዳይባል፣ ከሕዝቡ መካከል ተጠምቆ ቢሆን ኦሪትና ሐዲስ ተቀላቅለዋል እንዳይባል፣ አዲስ ልጅነት ለምታስገኘዋ የአዲስ ኪዳን ጥምቀት አርአያ ሊሆን ሕዝቡ ሁሉ ከተጠመቁ በኋላ እርሱ ደግሞ ተጠመቀ፡፡ ከሁሉ በላይ የሆነ ጌታ ከሕዝቡ በኋላ ተጠመቀ፡፡

ጌታችን ሲጠመቅ ሰማይ ተከፈተ (ያልተገለጠ ምሥጢር ተገለጠ)፡፡ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል መጥቶ አረፈበት፡፡ አብም ከሰማያት “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” አለ፡፡ አምላክ በተጠመቀ ጊዜ ዮርዳኖስ ሸሸች፤ ተራሮችም እንደ ኮርማዎች ኮረብቶችም እንደ በጎች ጠቦቶች ዘለሉ (መዝ. ፻፲፫፥፫-፮)፡፡

ሰዎች በእርሱ ስም ይጠመቃሉ፡፡ እርሱስ በማን ስም ተጠመቀ? ቢሉ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ስለሆነ መጥምቁ ዮሐንስ እንዴት ብሎ ማጥመቅ እንደሚችል ግራ ገብቶት “ሌላውን ሰው በአንተ ስም አጠምቃለሁ፤ አንተን በማን ስም አጠምቃለሁ?” ብሎ ጠይቆት ነበር፡፡ ጌታም “ወልዱ ለቡሩክ ከሣቴ ብርሃን ተሣሀለነ፤ አንተ ካህኑ ለዓለም በከመ ሢመቱ ለመልከጼዴቅ፤ የቡሩክ የእግዚአብሔር ልጅ፣ የብርሃን መገኛ ይቅር በለን፡፡ አንተ እንደ መልከጼዴቅ ለዓለም ካህን ነህ፡፡” ብለህ አጥምቀኝ እንዳለውና እንደዚሁ ብሎ አጥምቆታል ብለው መተርጉማን ያስተምሩናል፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ሲሆን ለምን መጠመቅ አስፈለገው?

፩. ጥምቀትን ለመመሥረት (ለመባረክ)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትን “ሰው ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገባም፡፡” እንዲሁም “ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያላመነ ግን ይፈረድበታል፡፡” በማለት በትምህርት፤ እንዲሁም ቅዱሳን ደቀ መዛሙርቱን “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ አጥምቁ፡፡” በማለትም በትእዛዝ እንደ መሠረተ፤ ፍጹም ሰው ሆኖ ጥምቀትን በተግባር ለመመሥረት ተጠመቀ፡፡ (ዮሐ. ፫፥፭፣ ማር. ፲፮፥፲፮) ጥምቀትን የድኅነት መሠረት አድርጎ ሠራት፡፡ በስደቱ ስደታችንን እንደባረከልን፤ በጸሎቱም ጸሎታችንን ተሰሚ እንዳደረገልን በመጠመቁም ጥምቀታችንን ባርኮ ቀድሶ ሰጠን፡፡ በአጠቃላይ ምሥጢረ ጥምቀትን ሊመሠርታትና ራሱ ተጠምቆ አርአያ ለመሆን ተጠመቀ፡፡

ሁላችን ለመጠመቅ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንሄድ ዘንድ ሊያስተምር በመጀመሪያ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ሄደ፡፡ እኛም ወደ ካህናት ሄደን እንድንጠመቅ አርአያ ለመሆን እርሱ አምላክ ሲሆን ወደ ፍጡሩ ወደ ዮሐንስ ለመጠመቅ ሄደ፡፡ ሁላችን በውኃ እንድንጠመቅ እርሱም በውኃ ተጠመቀ፡፡ ጥምቀት ለእኛም የክርስትና መግቢያ በር እንድትሆንልን ጥምቀትን የሥራው ሁሉ መጀመሪያ አደረጋት፡፡ እኛም ስንጠመቅ መንፈስ ቅዱስ እንደሚወርድልን ለማጠየቅ እርሱ ሲጠመቅ መንፈስ ቅዱስ ወረደ፡፡ እኛ በሥላሴ ስም እንድንጠመቅ ምሥጢረ ሥላሴ በዮርዳኖስ ተገለጠ፡፡ ጥምቀት አንዲትና የማትደገም ምሥጢር ናትና እርሱም አንድ ጊዜ ብቻ ተጠመቀ፡፡ “…እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው ጥምቀትና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን፡፡”  እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ፤ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊም “የሚመሰክሩት መንፈሱና ውኃው ደሙም እነዚህ ሦስቱ ናቸው፤ ሦስቱም አንድ ናቸው፡፡” በማለት እንደመሰከረ፤ እኛም ተጠምቀን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ፣ ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ተወልደን ልጆቹ እንሆን ዘንድ ጥምቀትን ሠራልን፡፡ (ቲቶ. ፫፥፬፣ ፩ዮሐ. ፬፥፰) በእርሱ ጥምቀት አማካይነት ጥምቀት ከሰማይ መሆኗን፤ በእግዚአብሔር ፈቃድ የምትደረግ መሆኗን አሳየን፡፡ ጥምቀታችንንም በጥምቀቱ ባረከልን፡፡

፪. አንድነት፣ ሦስትነት እንዲገለጥ

በጌታችን ጥምቀት አምላክ በዮርዳኖስ በአንድነት በሦስትነት ተገልጧል፡፡ አብ በሰማያት ሆኖ በመመስከር “የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት፡፡” በማለት፤ ወልድ ቅድመ ዓለም ከአብ የተወለደ የባሕርይ ልጁ መሆኑን፤ በተዋሕዶ የከበረ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑን ለማጠየቅ “ልጄ” ብሎ መሰከረ፡፡ ወልድ በማዕከለ ባሕር ሥጋን ተዋሕዶ በመገለጥ፤ ፍፁም አምላክ ፍፁም ሰው ሆኖ፤ እንደ ሰው ተጠምቆ (ሥጋን ተዋሕዷልና)፤ የሰው ልጅ የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ፤ ይመጣል ተብሎ ትንቢት የተነገረለትን በመሆኑ (በኩነተ ሥጋ) በመጠመቅ ገለጠው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ በርግብ አምሳል መጥቶ በራሱ ላይ አርፎ ለሰው እንዲታይ በርግብ አምሳል ሆኖ ተገለጠ። በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን፣ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንድንጠመቅ ይህንን ምሥጢር በዮርዳኖስ ገለጠልን። እግዚአብሔር አብ በደመና ሆኖ ስለ ባሕርይ ልጁ በመመስከር፣ እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ ፊት በትሕትና በመቆም፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በነጭ ርግብ አምሳል በመውረድ ከኢአማንያን ተሠውሮ የነበረ ሦስትነቱ ታወቀ፣ አስተርእዮ ሆነ፡፡

፫. ትሕትናን ለማስተማር

የጌታችን የትሕትናው ነገር እጅግ ድንቅ ነው፡፡ እርሱ ፈጣሪ ሲሆን ራሱ በፈጠረው ፍጡር በዮሐንስ እጅ ተጠምቀ፡፡ ንጹሐ ባሕርይ ሆኖ ሳለ ስለ ሰው ልጅ ሲል ጽድቅን ለመፈፀም ተጠመቀ፡፡ ሰማያዊው ንጉሥ በምድራዊው ሰው ተጠመቀ፡፡ እሳትነት ያለው መለኮትን ያለመለየት የተዋሐደ ሥጋ ፍጹም ሰው ሆኖ ተጠመቀ፡፡ በእሳትና በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቀው እርሱ በውኃ ተጠመቀ፡፡ ፍጡራን በስሙ የሚጠመቁት እርሱ በፍጡር እጅ ተጠመቀ፡፡ ፈጣሪ የሆነው ራሱ በፈጠረው ውኃ ተጠመቀ፡፡ የሰውን ልጆች ኀጢአት የሚያስወግድ እርሱ ራሱን ዝቅ አድርጎ ከኃጢአተኞች ጋር አብሮ ተቆጥሮ ተጠመቀ፡፡ ይህንን ሁሉ ያደረገው ትሕትናን ለማስተማር ነው፡፡ “ከእኔም ተማሩ፥ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና” በማለት እንዳስተማረን፡፡ (ማቴ. ፥፩፥፳)

፬. ትንቢቱና ምሳሌውን ለመፈጸም

ጌታችን በዮሐንስ ሊጠመቅ ሲመጣ አምላክነቱን በመንፈስ ቅዱስ የተረዳ መጥምቁ ዮሐንስ “እኔ በአንተ ልጠመቅ እሻለሁ፤ አንተ ወደ እኔ ትመጣለህን?” ብሎ በከለከለው ጊዜ መምህረ ትሕትና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “አሁንስ ተው፤ እንዲህ ጽድቅን ሁሉ ልንፈጽም ይገባናልና፡፡” ብሎ መልሶለታል፡፡ “ጽድቅን መፈጸም” ብሎ ጌታ የገለጠው ትንቢተ ነቢያትን ነው፡፡ በፈለገ ዮርዳኖስ በመጠመቅ የነቢያትን ትንቢት ፈጸመ፡፡ ነቢዩ አስቀድሞ “አንቺ ባሕር የሸሸሽ፣ አንቺም ዮርዳኖስ ወደ ኋላሽ የተመለስሽ ምን ሆናችኋል? እናንተም ተራሮች፣ እንደ ኮርማዎች፣ ኮረብቶችስ እንደ በጎች ጠቦቶች ለምን ዘለላችሁ? ከያዕቆብ አምላክ ፊት፣ ከእግዚአብሔር ፊት ምድር ተናወጠች፡፡” የተባለውና እንዲሁም “አቤቱ ውኆች አዪህ፤ ውኆች አይተውህ ፈሩ፤ የውኆች ጥልቆች ተነዋወጡ፣ ውኆቻቸውም ጮሁ፡፡” በማለት የተናገረውን ትንቢት ለመፈፀም በዮርደኖስ ተጠመቀ፡፡ (መዝ. ፻፲፫፥፫፣ መዝ. ፸፫፥፲፮)

ለምን በፈለገ ዮርዳኖስ ተጠመቀ?

በዮርዳኖስ ወንዝ መጠመቁም በብሉይ ኪዳን ብዙ ምሳሌዎች ያሉት ሲሆን የሚከተሉትን ለአብነት ያህል መመልከት ይቻላል፡፡

፩. ዮርዳኖስ መነሻው አንድ ሲሆን ከዚያ በደሴት የተከፈለ፤ ኋላም የሚገናኝ ነው፡፡ የሰው ዘሩ አንድ አዳም ነው፡፡ ኋላ ሕዝብና አሕዛብ ተብሎ በግዝረትና በቁልፈት ተከፈለ፡፡ በክርስቶስ ጥምቀት ሕዝብና አሕዛብ አንድ ሆኑ፡፡

፪. አባታችን አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ሲሄድ ካህኑ መልከ ጼድቅ ኅብስተ በረከት ጽዋዐ አኮቴት ይዞተ ቀብሎታል፡፡ አባታችን አብርሃም የምእመናን፣ ካህኑ መልከ ጼዴቅ የካህናት፣ ዮርዳኖስ የጥምቀት፣ ኅብስቱና ጽዋው የሥጋ ወደሙ ምሳሌ ናቸው፡፡ ዘፍ. ፲፬፥፲፪)

፫. ከሕዝብ ወገን የሆነው ጻድቁ ኢዮብ በዮርዳኖስ ተጠምቆ ከደዌ ሥጋ ድኗል፡፡ ከአሕዛብ ወገን የሆነውም ሶርያዊው ንዕማን በዮርዳኖስ ተጠምቆ ከደዌው ተፈውሶዋል፡፡ የሕዝብም የአሕዛብም ወገኖች በጥምቀት ከኀጢአት ይድናሉና ያን ለማጠየቅ፡፡ (፪ነገ. ፭÷፩-፲፭)

፬. እስራኤል ዘሥጋ ዮርዳኖስን ተሻግረው ምድረ ርስት ገብተዋል፡፡ ነቢዩ ኤልያስም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ ገነት ዐርጓል፡፡ ምእመናንም አምነው ተጠምቀው ገነት መንግሥተ ሰማያት ይገባሉና፡፡ (ኢያ. ፫፥ ፪ነገ. ፪)

፭. ፈለገ ዮርዳኖስ በክረምት አይሞላም፡፡ በበጋም አይጎድልም፡፡ በጥምቀትም የሚገኝ ልጅነት ጽኑዕ ነው፣ አይነዋወጥም፡፡

በፈለገ ዮርዳኖስ የመጠመቁ ምሥጢር

ጌታችን በዮርዳኖስ የተጠመቀበትን ምሥጢራዊ ምክንያት ሊቃውንቱ “የአዳምንና የሔዋንን (የሰው ልጆችን) የዕዳ ደብዳቤ ሊያጠፋ ነው፡፡” በማለት ይገልጡታል፡፡ አዳምና ሔዋን ዕፀ በለስን በልተው ከተሳሳቱ በኋላ ዲያብሎስ የጨለማ መጋረጃ ጋርዶ መከራ አጸናባቸው፡፡ በመከራቸውም ጊዜ “ስመ ግብርናችሁን ጽፋችሁ ብትሰጡኝ መከራችሁን አቀልላችሁ ነበር” አላቸው፡፡ “አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ (አዳም የዲያብሎስ ባሪያ ነው) ሔዋን አመቱ ለዲያብሎስ (ሔዋን የዲያብሎስ አገልጋይ ናት)” ብለው ጽፈው ሰጡት (ይሁንብን አሉ)፡፡ እርሱም በሁለት እብነ ሩካብ ጽፎ አንዱን በዮርዳኖስ አንዱንም በሲኦል ጥሎታል፡፡ በዮርዳኖስ ያለውን ጌታ ሲጠመቅ እንደ ሰውነቱ ረግጦ እንደ አምላክነቱ አቅልጦ አጥፍቶላቸዋል፡፡ በሲኦል ያለውን ደግሞ በዕለተ ዐርብ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ሲያወጣ አጥፍቶላቸዋል፡፡ ጌታችን በዮርዳኖስ የመጠመቁ ምሥጢራዊ  ምክንያት ይህንን የዕዳ ደብዳቤ ለማጥፋት ነው፡፡ (ሚክ. ፯፥፲፱፣ ቆላ. ፪፥፲፬)

ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጥምቀት ዕለት

ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን በጥምቀት ዕለት “ሖረ ኢየሱስ እምገሊላ ኀበ ዮርዳኖስ” (ኢየሱስ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ሄደ) ስትል ታቦታቱን ከመንበራቸው በማንሣት ወደ ጥምቀተ ባሕሩ በእልልታና በምስጋና ትወስዳለች፡፡ “…ቆመ ማዕከለ ባሕር…” እያለችም በመዘመር የጌታን ጥምቀት ታከብረዋለች፡፡ “…ተጠምቀ በማየ ዮርዳኖስ…. በእደ ዮሐንስ…” እያለች ታመሰግነዋለች፡፡ “ባሕርኒ ርእየት ወጎየት….” እያለችም የነቢያትን ትንቢት ፍፃሜ ትሰብካለች፡፡ በጥምቀተ ባሕር ያለውንም ውኃ በመባረክ፤ ምእመናንንም በተባረከው ውኃ በመርጨት ከበዓሉ በረከት እንዲቀበሉ ታደርጋለች፡፡ ይህ ዳግመኛ ጥምቀት አይደለም፡፡ በዚህ ዕለት በዋናነት በዮርዳኖስ የተጠመቀው አምላክ የሚመሰገንበት ቀን ነው፡፡ ለእርሱም በማሕሌት፣ በመዝሙር፣ በቅዳሴ ምስጋና የሚቀርብበት ቀን ነው፡፡ የጥምቀት በዓል ሁላችንም የምንባረክበትና በረከትን የምናገኝበት ዕለት ነው፡፡

የእግዚአብሔር አምላክ ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን