ፅንሰታ ለማርያም

ቅደስት ቤተ ክርስቲያናችን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችበትን ዕለት ነሐሴ ፯ ቀን በየዓመቱ በድምቀት ታከብረዋለች፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላጆች በእናቷ ሐና በኩል ቅድመ አያቶቿ ጴጥሪቃና ቴክታ ደጋጐችና እግዚአብሔርን የሚፈሩና በፍጹም ልቡናቸው እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ነበሩ፡፡

እግዚአብሔርን ማምለክ ብቻ ሳይሆን በባለጠግነታቸውም የታወቁ ነበሩ፡፡ ነገር ግን ልጅ ስላልነበራቸው በጣም ያዝኑና ይተክዙ ስለነበር አንድ ቀን ጰጥሪቃ የሀብቱን ብዛት ተመልክቶ ሚስቱን (ቴክታ)ን “ያለን ገንዘብና ንብረት እንኳን ለእኛ ለልጅ ልጆቻችን የሚተርፍ ነው፡፡ ነገር ግን ወራሽ ልጆች የሉንም” እያለ በትካዜ ተናገራት፡፡ ቴክታም ከእርሷ ልጅ ባለመውለዱ ሌላ ወላድ ሴት የፈለገ መስሏት ‘እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ነውና ሌላ አግብተህ ወለድ” አለቸው በትካዜ ውስጥ ሆና፡፡  

ጴጥሪቃም “ይህንንስ በልቤ እንዳላሰብኩና እንዳልተመኘሁ እግዚአብሔር ያውቃል” በማለት ተናገራት፡፡ ቴክታም በሐዘን ወስጥ ሆና ሳለች ራእይ ታያለች፤ ነጭ እንቦሳ ከማሕኅፀኗ ስትወጣ፤ እንቦሳዪቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ሰባት ስትደርስ፣ ሰባተኛዋ ጨረቃን ስትወልድ፤ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ አየች። እርሷም ባየችው ራእይ ተገርማ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ አደነቀች፡፡ “በሕልሜ ነጭ ጥጃ ከማኅፀኔ ስትወጣ፣ ያችም ነጭ ጥጃ ደግሞ ነጭ ጥጃ ስትወልድ፣ እንደዚህ እየሆነ እስከ ሰባት ትውልድ ሲደርሱ ሰባተኛዪቷም ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋ ደግሞ ፀሐይን ስትወልድ አየሁ” በማለት አስረዳችው።

ጰጥሪቃም ባለቤቱ ባየችው ራእይ ተደንቆ ሕልም ለሚፈታ ሰው የሚስቱን ራእይ ተናገረ፡፡ ሕልም ተርጓሚውም ምስጢር ተገልጾለት “ሰባት አንስት ጥጆች መውለዳችሁ ሰባት ሴቶች ልጆች ይወለዳሉ፤ ነጭ መሆናቸው ደጋጎች ልጆች መሆናቸውን ሲያመለክት፤ ሰባተኛዪቱ ጨረቃን መውለዷ ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ናት፤ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም” በማለት ተረጐመለት፡፡ ጰጥሪቃም በተተረጎመለት ራእይ ተገርሞ ለሚስቱ ነገራት፤ እርሷም “የእስራኤል አምላክ የሚያደርገውን እርሱ ያውቃል” በማለት ፈጣሪዋን አመሰገነች፡፡

ቴክታ ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ሔሜን አሏት፤ ሔሜን – ዴርዴን ወለደች፤ ዴርዴም – ቶናን፤ ቶናም – ሲካርን ወለደች፤ ሲካርም – ሴትናን፤ ሴትናም – ሔርሜላን ወለደች፤ ሔርሜላም የተከበረችና የተመረጠች ዓለሙን ሁሉ ለፈጠረ ጌታ አያት ለመሆን የበቃችውን ሐናን ወልዳለች። ሐና በመልካም አስተዳደግ አድጋ አካለ መጠን ስታደርስ ከነገደ ይሁዳ ከመንግሥት ወገን የተወለደ የቅስራ ልጅ የአልዓዛር የልጅ ልጅ ከሚሆን ከኢያቄም ጋራ አጋቧት፡፡ ሁለቱም ወደ ቤተ እግዚአብሔር ዕለት ዕለት በመሄድ ለዐይናቸው ማረፊያ ለልባቸው ተስፋ የሚሆን ልጅ እንዲሰጣቸው ይለምኑ ነበር፡፡

ከዕለታት በአንደኛው ቀን ሁለቱም ወደ ቤተ እግዚአብሔር ሄደው ሲጸልዩ ውለው ሲመለሱ ርግቦች ከልጆቻቸው ጋር ደስ ብሏቸው ሲጫወቱ አይተው ሐና “አቤቱ ጌታዬ ግዕዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሣኸኝ?” ብላ ምርር ብላ አለቀሰች፡፡ ወዲያው ሳይውሉ ሳያድሩ ሱባኤ ይገባሉ፤ ኢያቄም ወደ በረሃ ሄዶ ሲጸልይ ሐና ደግሞ በቤቷ ዙሪያ ባለው የአትክልት ቦታ ሱባኤ ያዘች፤ በሱባኤያቸው ፍጻሜም ሁለቱም ራእይ አይተው ተነጋግረዋል፡፡

ኢያቄም “ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ወፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ብሎ የተገለጸለትን ለሐና ነግሯታል፤ ይኸውም የራእዩ ምስጢር፡- ወፍ የተባለው አካላዊ ቃል ክርስቶስ ሲሆን፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባሕርዩ ነው፤ ከላይ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየሁ ማለቱ የኢያቄምን ባሕርይ ባሕርይ እንደሚያደርግ ሲያጠይቅ ሲሆን፤ ሰባቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ምልአቱ፣ ስፍሐቱ፣ ርቀቱ፣ ልዕልናው፣ ዕበዩ ናቸው፡፡

ሐናም ተገልጾላት ለባሏ “ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በጆሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ” አለችው። ምስጢሩም፡- ርግብ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትሆን፤ ነጭነቷ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ዘላለማዊ ድንግልናዋ ነው፤ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ ወደ ዦሮዬ ገብታ በማኅፀኔ ስትተኛ አየሁ ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በዦሮዋ ሰምታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን የምትፀንሰውን ንጽሕት ርግብ የተባለችውን እመቤታችንን የምትወልድ መሆኗን ሲያጠይቅ ነው፡፡

ኢያቄምና ሐናም ይህንን ራእይ ሐምሌ ፴ ቀን ካዩ በኋላ “ወንድ ልጅ ብንወልድ ወጥቶ ወርዶ ይርዳን አንልም ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ይሆናል፤ ሴትም ብንወልድ ለቤተ እግዚአብሔር መጋረጃ ፈትላ ትኑር” ብለው ስእለት ከተሳሉ በኋላ ራእይ አየን ብለው ዕለቱን አልተገናኙም፤ አዳምንና ሔዋንን “ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሏት” ብሎ የተናገረው አምላክ ለእኛም ይግለጽልን ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ ሰባት ቀን ድረስ ለየብቻቸው ሰነበቱ።

ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን “ከሰው የበለጠች ከመላእክት ሁሉ የከበረች ልጅ ትወልዳላችሁ” ብሎ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለሐና ነግሯት በፈቃደ እግዚአብሔር በብሥራተ መልአክ እመቤታችን ነሐሴ ሰባት ቀን እሑድ ተፀንሳለች፡፡ ለዓለም ሁሉ የድኅነት መገኛ የሆነች ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችበት ዕለት ነሐሴ ሰባት የተባረከች እንደመሆኗ መላው ክርስቲያን በዓሏን ሊያከብር ይገባል፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በከበሩ ኢያቄምና ሐና ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸው ከእኛ ጋር ይኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ከመጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ነሐሴ

       መጋቤ ሐዲስ ዶ/ር ሮዳስ ታደሰ፣ ነገረ ማርያም በሐዲስ ኪዳን

የጾመፍልሰታየዕለታትምንባባት፣ ምስባክ፣ ወንጌልና ቅዳሴ

ነሐሴ ፩

ምንባባት

. ፩ኛጢሞ. ፭ ፥፲፩

. ፩ኛዮሐ. ፭፥ ፩-፮

. ግብ.ሐዋ. ፭ ፥፳፯-፴፬

ምስባክ

. ወእነግር ስምዐከ በቅድመ ነገሥት ወኢትይኀፈር፤

ወአነብብ ትእዛዘከ ዘአፍቀርኩ ጥቀ፤

ወአነሥእ እደውየ ኀበ ትእዛዝከ ዘአፈቅር

ወንጌል

. ዮሐ. ፲፱፥፴፰-ፍጻሜ

ቅዳሴ 

. ዘዮሐንስ አፈወርቅ አው ዘእግዝእትነ

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛጢሞ. ፪፥፰-ፍጻሜ 

. ፩ኛጴጥ. ፫፥፩-፮

. ግብ.ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

ምስባክ

. ወይወስዱ ለንጉሥ ደናግለ ድኅሬሃ፤

ወቢጻሂ ይወስዱ ለከ፤

ወይወስድዎን በትፍሥሕት ወበሐሤት፤

ወንጌል 

. ዮሐ. ፰፥፱-፲፪

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛተሰ. ፩፥፩-ፍጻሜ

. ፩ኛ ጴጥ. ፫፥ ፲-፲፭

. ግብ. ሐዋ. ፲፬፥፳-ፍጻሜ

ምስባክ

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤

ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤

ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፤

ወንጌል 

. ሉቃ. ፲፰፥፱-፲፰

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ሮሜ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ

. ፩ ጴጥ. ፭፥፲፪

. ሐዋ. ፲፯፥፳፫-፳፰

ምስባክ

. እግዚኦ በኃይልከ ይትፌሣሕ ንጉሥ፤

ወብዙኃ ይትሐሠይ በአድኅኖትከ፤

ፍትወተ ነፍሱ ወሀብኮ፡፡

ወንጌል 

. ሉቃ. ፲፬፥፴፩-ፍጻሜ

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘቄርሎስ

ነሐሴ

ንባባት

. ፪ኛቆሮ. ፲፪፥፲-፲፯

. ፩ኛዮሐ. ፭፥፲፬-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፲፭፥፩-፲፫

ምስባክ

. ወትሰይመኒ ውስተ ርእሰ ሕዝብ፤

ሕዝብ ዘኢየአምር ተቀንየ ሊተ፤

ውስተ ምስማዐ ዕዝን ተሠጥዉኒ፤

ወንጌል

. ሉቃ. ፲፭፥፩-፲፩

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፫፥፲-፳፪

. ፩ኟ ጴጥ. ፫-፯

. ግብ.ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

ምስባክ

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ፤

ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር፤

ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን፡፡

ወንጌል

. ማር. ፲፮፥፱-፲፱

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ

ምንባባት

. ዕብ. ፩፥፩-፲፯

. ፩ኛጴጥ. ፪፥፯-፲፰

. ግብ.ሐዋ. ፲፥፩-፴

ምስባክ

. ብፁዕ ብእሲ ዘአንተ ገሠጽኮ እግዚኦ፤

ወዘመሀርኮ ሕገከ፤

ከመ ይትገኀሥ እመዋዕለ እኩያት፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፲፮፥፲፫-፳፬

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

ሮሜ. ፱፥፳፬- ፍጻሜ

፩ኛጴጥ. ፬፥፲፪-ፍጻሜ  

ግብ. ሐዋ. ፲፮፥፴፭-ፍጻሜ

ምስባክ

. ወድቀት እሳት ወኢርኢክዋ ለፀሐይ፤

ዘእንበለ ይትዐወቅ ሦክክሙ ሕለተ ኮነ፤

ከመ ሕያዋን በመዓቱ ይውኅጠክሙ፡፡

ወንጌል

. ማቴ. ፯፥፲፪-፳፮

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ

ምንባባት

. ፊልጵ. ፩፥፲፪-፳፬

. ፪ኛዮሐ. ፩፥፮-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፲፭፥፲፱-፳፭

ምስባክ

. ወትቀውም ንግሥት በየማንከ፤

በአልባሰ ወርቅ ዑፅፍት ወሑብርት፤

ስምዒ ወለትየ ወአጽምኢ እዝነኪ፡፡

ወንጌል 

. ዮሐ. ፲፥፩-፳፪

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘባስልዮስ

ነሐሴ ፲
ምንባባት

. ዕብ. ፲፪፥፳፪- ፍጻሜው 

. ፩ኛጴጥ. ፩፥፮-፲፫ 

. ግብ.ሐዋ. ፬፥፴፩-፳፭ 

ምስባክ

. ተዘከር ማኅበረከ በትረ ርስትከ፤

ወአድኀንከ በትረ ርስትከ፤
ደብረ ጽዮን ዘኀደርከ ውስቴታ፡፡

ወንጌል

. ሉቃ. ፲፮፥፱-፲፱ 

ቅዳሴ 

ዘእግዝእትነ ማርያም 

ነሐሴ ፲፩
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፭፥፲፩-ፍጻሜ  

. ፩ኛዮሐ. ፪ ቊ. ፲፬-፳ 

. ግብ. ሐዋ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜው 

ምስባክ

. ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ፤

ወትሠይሚዮሙ መላእክተ ለኵሉ ምድር፤
ወይዘክሩ ስመኪ በኵሉ ትውልደ ትውልድ፡፡

ወንጌል

.ሉቃ. ፮፥፳-፳፬ 

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ ማርያም

ነሐሴ ፲፪
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፱፥፲፯-ፍጻሜ

. ይሁዳ. ቊ. ፰-፲፬ 

. ግብ.ሐዋ. ፳፬፥፩-፳፪ 

ምስባክ

. እግዚኦ ኩነኔከ ሀቦ ለንጉሥ፤

ወጽድቀከኒ ለወልደ ንጉሥ፤
ከመ ይኰንኖሙ ለሕዝብከ በጽድቅ፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፳፪፥፩-፲፭ 

ቅዳሴ

. ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ

ነሐሴ ፲፫
ምንባባት

. ዕብ. ፲፩፥፳፫-፴ 

. ፪ኛጴጥ. ፩፥፲፭ 

. ግብ.ሐዋ. ፯፥፵፬-ፍጻሜ

ምስባክ

. ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ፤

ወይሴብሑ ለስምከ፤
መዝራዕትከ ምስለ ኃይል፡፡

ወንጌል 

. ሉቃ. ፱፥፳፰-፴፰ 

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዲዮስቆሮስ፡፡

ነሐሴ ፲፬
ምንባባት

. ፩ኛቆሮ. ፩፥፲-፲፪ 

. ያዕ. ፩፥፲፪ 

. ግብ.ሐዋ. ፲፥፴-፵፬ 

ምስባክ

. ዘአዘዝከ መድኃኒቶ ለያዕቆብ፤

ብከ ንወግዖሙ ለኵሎሙ ፀርነ፤
ወበስምከ ናኃሥሮሙ ለእለ ቆሞ ላዕሌነ፡፡

ወንጌል 

. ማቴ. ፲፯፥፲፬-፳፬ 

ቅዳሴ 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈወርቅ

ነሐሴ ፲፭

ምንባባት        

. ፩ኛቆሮ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ   

. ይሁዳ. ፩፥፲፯-ፍጻሜ

. ግብ.ሐዋ. ፩፥፲፪-፲፭

ምስባክ   

. ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ፤

ቅዳሴ፡      

. ዘሐዋርያት

ነሐሴ ፲፮

ምንባባት       

. ሮሜ. ፰፥፴፩-ፍጻሜ   

. ዮሐ. ፪፥፩—፯  

. ግብ.ሐዋ. ፩፥፲፪-፲፭

ምስባክ፡   

. ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል፤

እግዚአብሔር ውስተ ማዕከላ ኢትትሐወክ፤

ወይረድኣ እግዚአብሔር ፍጽመ፡፡

ወዓዲ ወተዚያነዉ ዳኅናሃ ለኢየሩሳሌም፤

ወፍሥሐሆሙ ለእለ ያፈቅሩ ስመከ፤

ይኩን ሰላም በኃይልከ፡፡

ወንጌል

. ማቴ. ፳፮፥፳፮-፴፩

ቅዳሴ      

. ዘእግዚእነ

ጾመ ፍልሰታ ለማርያም

እንኳን ለፍልሰታ ለማርያም ጾም በሰላም አደረሳችሁ!

ጾመ ፍልሰታ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከደነገገቻቸው ሰባቱ የዐዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡ ይህንንም ጾም ከነሐሴ ፩-፲፮ ቀን ድረስ ለሁለት ሱባኤ ከሰባት ዓመት ሕፃናት ጀምሮ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ የሚጾሙትና በናፍቆት የሚጠበቅ ጾም ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያትን አብነት አድርጋ የምትጾመው ጾም እንደመሆኑ ምእመናን በየገዳማቱና አድባራት በመገኘት ራሳቸውን ለእግዚአብሔር በማስገዛት በሱባኤ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደትና በምሕላ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ያገኙ ዘንድ በፍጹም ፍቅርና ትጋት ይጾሙታል፡፡  

ፍልሰታ የሚለው ቃል “ፈለሰ” ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም “መለየት፣ ማረግ፣ ወደ ላይ መውጣት፣ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መሄድ” ማለት ነው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በ፷፬ ዓመቷ ከዚህ ዓለም ድካም ጥር ፳፩ ቀን ፵፱ ዓ.ም በማረፏ  ሐዋርያት ሥጋዋን በጌቴሴማኒ ለማሳረፍ ሲወስዷት አይሁድ “እንደ ልጇ ተነሣች፤ ዐረገች እያሉ እንዳያውኩን በእሳት እናቃጥላት” ብለው በዓመፃ ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም በክፋት ተነሣስቶ አጎበሩን ይዞ ሊያወርዳት ሲል የእግዚአብሔር መልአክ ሁለት እጆቹን ቆረጠው፡፡ እግዚአብሔርም ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ እመቤታችንን በደመና ነጥቆ  ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡ ዮሐንስም በዕፀ ሕይወት ላሉት ነፍሳት “ዛቲ ይእቲ ሕይወትክሙ ኪያሃ ሰብሑ፤” ብሎ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ተቀብለው “ብፅዒት ከርስ እንተፆረትኪ ወብፅዓት ዓይንት እለእርያ ኪያኪ ፤ ሕይወታችሁ ይህቺ ናት፤ እርሷን አመስግኑ፣ አንቺን የተሸከመች ማኅፀን የተባረከች ናት፤ አንቺን ያዩ ዓይኖችም የተባረኩ ናቸው ፤” ብለው አመስግነዋታል፡፡ “ትውልድ ዘኢይሀልፍ ያመሰግኑኛል” ማለት ይህ ነው፡፡  

ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ሐዋርያቱ በተመለሰ ጊዜ ሐዋርያቱ “እመቤታችንስ?” እያሉ በጥያቄ አፋጠጡት፡፡ እርሱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገነት በዕፀ ሕይወት እንዳስቀመጣት ነገራቸው፡፡ እነርሱም ዮሐንስ ያየውን እኛም ማየት አለብን ብለው ከነሐሴ ፩-፲፬ ሱባኤ ገቡ፡፡ ጌታችንም የሐዋርያቱን ጽናት ፍቅር ተመልክቶ የእመቤታችንን ትኩስ ሥጋ ከዕፀ ሕይወት አምጥቶ ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ተቀብለው በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡ በሦስተኛውም ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ ሕንድ በደመና ተጭኖ ሲመጣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በመላእክቱ ታጅባ ስታርግ ተገናኙ፡፡ ሐዋርያው ቶማስም ሐዋርያት ያዩትን እኔ ሳላይ ብሎ አዘነ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?” በማለት ከደመናው ወደ መሬት ራሱን ሊጥል ሲቃጣው እመቤታችን ማረጓን እርሱ ብቻ እንደተመለከተ ነግራ የተገነዘችበትን ሰበን ሰጥታው ዐረገች፡፡  

ሐዋርያው ቶማስ ወደ ሐዋርያት በተመለሰ ጊዜም “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው፡፡ እነርሱም “አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆናል?” አላቸው፡፡ ከሐዋርያት መካከል ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ በፊት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ ተጠራጥሮ እንደነበር በመግለጽ ገሰጸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ተቈጥቶ የእመቤታችንን ክቡር ሥጋ ለቅዱስ ቶማስ ለማሳየት ሔዶ መቃብሯን ቢከፍት የእመቤታችንን ሥጋ ሊያገኘው አልቻለም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ቆመ፡፡

ቅዱስ ቶማስም “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ስታርግ አግኝቻታለሁ” ብሎ የሰጠችውን ሰበን ለሐዋርያት ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት እየተደሰቱ ሰበኑን ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን በቅዳሴ ጊዜ ሠራዒ ዲያቆኑ በሚይዘው መስቀል ላይ የሚታሠረው መቀነት መሰል ልብስ፤ እንደዚሁም አባቶች ካህናት በመስቀላቸው ላይ የሚያደርጉት ቀጭን ልብስና በራሳቸው የሚጠመጥሙት ነጭ ሻሽ የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡

ሐዋርያትም ቶማስ ያየውን እውነት ለማየትና ከእመቤታችን በረከት ለማግኘት ከነሐሴ ፩-፲፮ በጾምና በጸሎት ተወስነው ቆይተዋል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታቸውን ሰምቶ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችንን መንበር፤ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፤ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ እመቤታችንንም ሐዋርያትንም አቍርቧቸዋል፡፡ እነርሱም እመቤታችንን በዓይናቸው ከማየት ባሻገር አብረው ሥጋውን ደሙን ተቀብለዋል /ትርጓሜ ውዳሴ ማርያም/፡፡ እንደ ልጇ እንደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ትንሣኤ” ያሰኘውም ይህ ታሪክ ነው፡፡

በጾመ ፍልሰታ በቤተ ክርስቲያናችን በየቀኑ በማኅሌቱ፣ በሰዓታቱና በቅዳሴው በሚደርሰው ቃለ እግዚአብሔር ነገረ ማርያም ማለትም የእመቤታችን ከመፀነሷ ጀምሮ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለው ታሪኳ፣ ለአምላክ ማደሪያነት መመረጧ፣ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ክብሯ፣ ርኅርራኄዋ፣ ደግነቷ፣ አማላጅነቷ፣ ሰውን ወዳድነቷ በስፋት ይነገራል፡፡ እመቤታችንን ከሚያወድሱ ድርሳናት መካከልም በተለይ ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከነገረ ማርያም ጋር በማዛመድ የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም፤ እንደዚሁም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌ (ከነገረ ክርስቶስ) እና ከነገረ ማርያም ጋር በማመሣጠር የሚያትተው ውዳሴ ማርያምም በስፋት ይጸለያል፤ ይቀደሳል፤ ይተረጐማል፡፡ በሰንበታት የሚዘመሩ መዝሙራት፤ በየዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለተዋሕዶ በእግዚአብሔር መመረጧን፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን፣ ክብሯን፣ ቅድስናዋን፣ ንጽሕናዋን የሚያወሱ ናቸው፡፡

ምእመናንም በረከት ያገኙ ዘንድ የዲያብሎስንም ፈተና ድል ይነሡ ዘንድ ከነሐሴ ፩-፲፮ ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው በየገዳማቱና በየአብያተ ክርስቲያናቱ በዓት አዘጋጅተው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው አስገዝተው ይጾማሉ፤ ይጸልያሉ፤ እንደዚሁም ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ይህ ጾም ለእመቤታችን ያለንን ፍቅር የምንገልጽበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ኦርቶዶክሳውያን ሕፃናት ከሌላው ጊዜያት በተለየ ሁኔታ ትምህርተ ወንጌል የሚማሩት፤ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሚቀበሉት በዚህ በጾመ ፍልሰታ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋና በረከት አይለየን፡፡

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፤

በሀገራችን በኢትዮጵያና በመላው ዓለም የምትገኙ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፡-

የክብር ባለቤት እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ ሰባት ዓ.ም የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ!

‹‹ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፤ ነፍሴ እግዚአብሔርን እጅግ ታከብረዋለች›› (ሉቃ. ÷፵፮)

ይህንን ዐረፍተ ነገር የተናገረችው ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በሠራው ስሥራ ሰውነታችንን ለመዋሐድ የመረጣት ምርጥ የፍጥረት ወገን ናት፤ ፍጥረት ሁሉ በእግዚአብሔር ለእግዚአብሔር ተፈጥሮአል፤ የእግዚአብሔርም ነው፤ የቅድስት ድንግል ማርያም መመረጥም በእግዚአብሔር ለሰው የተደረገ ምርጫ ነው፤

የሰው መዳን ከጥንቱ ከጠዋቱ በእግዚአብሔር ልዩ አሠራር እንደሚከናወን በነቢያት የተገለጸ ነበረ፣ ‹‹አኮ በተንባል ወአኮ በመልአክ አላ ለሊሁ እግዚእ ይመጽእ ወያድኅነነ፤ በአማላጅም አይደለም፤ በመልአክም አይደለም እሱ ራሱ ጌታ መጥቶ ያድነናል እንጂ›› የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ትንቢትም ይህንን ያስረዳል፤ ቃለ ትንቢቱ ድኅነታችን በጌታ ቤዛነት እንደሚከናወን ያረጋግጣል፤ ይህም ሊሆን የቻለው ከፍጡራን ወገን በደሙ ቤዛነት ፍጡራንን የሚያድን ስለሌለ ነው፤

ከዚህ አንጻር የሰው መዳን በእግዚአብሔር አሠራር በደም ቤዛነት ከሆነ፣ በደሙ ቤዛነትም ዓለምን ማዳን የሚችል ከፍጡር ወገን ከሌለ፣ መዳናችን በእግዚአብሔርና በእግዚአብሔር እጅ ብቻ የተንጠለጠለ ነበረ፤ እግዚአብሔር በደሙ ቤዛ ሆኖ ዓለምን ለማዳን ደግሞ ደም ሊኖረው ይገባ ነበር፤ በመሆኑም እግዚአብሔር በክዋኔው ደም የሌለው ስለሆነ ለቤዛ ዓለም የሚፈስ ደምን ገንዘብ ማድረግ ነበረበት፤ ይህንን ደም ለመዋሐድ ቅድስት ድንግል ማርያምን መረጠ፤ ለዚህ ብቁ እንድትሆንም በእስዋ ላይ ሥራውን ሥራ፤ በምርጫውም መሠረት ከቅድስት ድንግል ማርያም ደማዊ ሥጋንና ነፍስን ተዋሕዶ ለቤዛዊ መሥዋዕት መንገዱን አመቻቸ፤

ቅድስት ድንግል ማርያም በነገረ ድኅነት መሰላል ለመሆን በእግዚአብሔር የተመረጠች በመሆኗ አንቀጸ አድኅኖ ወይም የድኅነት በር ትባላለች፤ ቅድስት ድንግል ማርያም ለዚህ ታላቅ ነገረ ድኅነት መመረጥዋ እጅግ ታላቅ ዕድል መሆኑን ስለተገነዘበች ‹‹ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና›› በማለት እግዚአብሔርን በመዝሙር አመስግናለች አክብራለችም፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

የቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና እና የአምልኮ መዝሙር የኛም መዝሙር ነው፤ እግዚአብሔር ለቅድስት ድንግል ማርያም ታላላቅ ሥራዎችን እንደሠራ ለኛም ብዙ ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልናል፤ እየሠራልንም ነው፤ ለሠራልን አምላክም እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም ታላቅ ክብርን መስጠት ይገባናል፤ ለእግዚአብሔር የምንሰጠው ክብርም በቃል ብቻ የሚገለጽ ሳይሆን በተግባር የሚታይ ሊሆን ይገባል፤ የድንግል ማርያም መንፈሳዊ ሕይወት በማስተዋል በትሕትና፣ በትዕግሥት በርኅራኄ በመታዘዝ በንጽሕና በቅድስና በክብርና በበረከት የተሞላ እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ከተጻፈው ሥነ ሕይወቷ መረዳት እንችላለን፤ ታድያ በእርሷ ክብርና ተማሕፅኖ የምንተማመን ልጆቿም የእሷን ያህል እንኳ ባንችል ወደ እርስዋ የሚጠጋጋ መንፈሳዊ ሕይወት ሊኖረን ይገባል፤ ይህም የምናደርገው ለእግዚአብሔር ክብርና ለእኛ መዳን ሲባል ነው፤ እኛ እግዚአብሔርን ስናከብር እንከብራለን እንድንማለን፤ ለእግዚአብሔር ክብር የማንሰጥ ከሆነ ግን ውጤቱ መክበር ሳይሆን ሌላ ነው የሚሆነው፤

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

እኛ በየጊዜው ጾምን እንድንጾም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት ፈቃደ ሥጋችንን በመግራት ለእግዚአብሔር ታዛዦች እንድንሆን ነው፤ ጾም የኃጢኣት መግቻ መሣሪያ በመሆኑ ‹‹ልጓመ ኃጢኣት›› ተብሎ ይታወቃል፤ በዚህም ሰውነታችንን ለግብረ ኃጢአት ከሚያጋግሉ ምግቦች አርቀን በሰከነ መንፈስ እግዚአብሔርን እያሰብን ኃጢአታችንንም እያስታወስን በንስሓ ወደ እርሱ ለመቅረብና ለሱ ለመታዘዝ እንጾማለን፤

የጾም ጥቅም ከጥንት ጀምሮ የታወቀ በእግዚአብሔርና በሰውም ተቀባይነት ያለው ነው፤ እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ መታዘዝን ይወዳልና በጾምና በጸሎት ለሱ ልንታዘዝ ይገባል፤ እግዚአብሔር በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ሊያድር የቻለው ‹‹እንዳልኸኝ ይሁንልኝ›› ብላ ታዛዥነትዋን በገለጸች ጊዜ ነው፤ እኛም እንዳልከን ይሁንልን እያልን እንደ እስዋ ታዛዥ መሆን አለብን፤

ዛሬ በዓለማችን ያለው መተረማመስ ለእግዚአብሔር ያለመታዘዝ ያመጣው ጣጣ እንደሆነ ማንም አይስተውም፤ መታዘዙ ቢኖር ኖሮ የሰው ልጅ ሰውን የሚያድን ብቻ እንጂ ሰውን የሚገድል መሣሪያ አያመርትም ነበር፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ወንድምህን እንደ ራስህ አድርገህ ውደድ አለ እንጂ ግደል ብሎ አላዘዘምና ነው፤ አሁንም በዚህ ባለንበት ዓለም በጣም ተባብሶ የሚገኘው የመጠፋፋት ዝንባሌ ለእግዚአብሔር በመታዘዝ በሰላምና በሰጥቶ መቀበል ካልተቋጨ ዳፋው አስከፊ መሆኑ አይቀርም፤

ከዚህ አንጻር ዛሬም ለሰው ልጆች ሁሉ የምናስተላልፈው መልእክት ‹‹በፍቅር ከሆነ ትንሹም ለሁሉ ይበቃልና ያለውን በጋራ በመጠቀም በፍቅርና በሰላም እንኑር›› የሚል ነው፤ ‹‹ፍትሕና ርትዕም ለሰው ልጅ መነፈግ የበለትም፤ ሰው በምድር ላይ ሠርቶ የመኖር መብቱ ሊከበርለት ይገባል፤ ይህንን ማድረግ ማለት ለእግዚአብሔር መታዘዝ ማለት ነው፤ ስለሆነም ለእግዚአብሔር ክብርና ለራሳችን መዳን ስንል ለእርሱ በመታዘዝ በሕይወትና በሰላም እንኑር፡፡

በመጨረሻም፡

በጾመ ማርያም ሱባኤ ስለ ሀገር ሰላምና ስለ ሕዝብ ደኅንነት በመጸለይ፣ በልዩ ልዩ ምክንያት በመከራ ላይ ወድቀው የሚገኙ ወገኖቻችንን በሚያስፈልጋቸው ሁሉ በመርዳት ሱባኤውን እንድናሳልፍ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን እናስተላልፋለን፤

መልካም የሱባኤ ወቅት ያድርግልን፤ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

ነሐሴ 1 ቀን 2017 .

ዋሽንግተን ዲሲ

“እናቴ ሆይ ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ”

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ላይ ተመሥርታለችና ዙሪያዋን በከበቧት ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን መላእክት፣ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ተጋድሎና ጸሎት የታጠረች ናት፡፡ “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤ በተራራ ላይ የተሠራች ከተማ መሰወር አይቻላትም” (ማቴ. ፭፥፲፬) እንዲል መጽሐፍ ቅዱስ ቅዱሳንን በብርሃን ይመስላቸዋል፤ ቅዱሳን ወንጌልን በመስበክ ዓለምን አጣፍጠዋታልና፡፡

ቤተ ክርስቲያን ለእነዚህ ዓለምን ድል ለነሱ ቅዱሳን ከዓመት እስከ ዓመት የተወለዱበትን፣ ተአምራት ያደረጉበትንና ያረፉበትን ቀን አስልታ መታሰቢያቸውን በድምቀት ታከብራለች፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት መካከል ደግሞ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ንጉሡ ለሚያመልከው ጣኦት አንሰግድም በማለታቸው መከራ የተቀበሉበትና በእምነታቸው ጽናት እግዚአብሔርን ደስ በማሰኘታቸው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከነደደው እሳትና የፍላቱ ኃይል ዐሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደ ላይ ከሚዘል የፈላ ውኃ ያዳነበትን ቀን ሐምሌ ፲፱ ቀን አስባ በድምቀት ታከብራለች፡፡

በቤተ ክርስቲያን በየዕለቱ ከሚነበቡ መጻሕፍት መካከልም ስንክሳር ታሪኩን እንዲህ ይተርከዋል፡፡

ቅድስት ኢየሉጣ በሮም ግዛት በሚገኝ አንጌቤን በሚባል አገር በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በክርስትና ሃይማኖት እና በበጎ ምግባር ጸንታ ትኖር የነበረች ደግ ሴት ናት፡፡ በሥርዓት ያሳደገችው ቂርቆስ የሚባል የሦስት ዓመት ሕፃን ልጅም ነበራት፡፡ ይህቺ ቅድስት የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራቷ ከልጇ ጋር ከሮም ወደ ጠርሴስ በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡

የንጉሡ ወታደሮችም እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን አስፈራሯቸው፡፡ ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኃ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡

በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡

አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም “እናቴ ሆይ! ገድላችን እንፈጽም ዘንድ ጨክኝ በርቺ አትጠራጠሪ” እያለ ቅዱስ ቂርቆስ እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን እንድትጸና አበረታታት፡፡ የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡ እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አስነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲሆን፣ መኰንኑ በተአምራቱ ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡

ዳግመኛም በፈላ የጋን ውኃ ውስጥ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ፤አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ ከፈላ

 ውኃ ያድነናል እያለ ያረጋጋት፣ በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡

ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ውኃውን እንደ ውርጭ አቀዘቀዘው፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ አስገብተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል አድኗቸዋል፡፡ በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡

እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ እናቴ ሆይ አትፍሪ እያለ በእሳት ውስጥ ሊጣሉ ባሉበት ወቅት እናቱን እንድትጸናና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ሁሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል አይዞህ! አይዞሽ! አትፍራ! አትፍሪ በመባባል በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ ታግሠን፣ እስከ ሞት ድረስ በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር ይገባናል፡፡

ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይሆን በጋራ ዋጋ የሚያገኙበት የድኅነት በር ነውና፡፡ ከዚሁ ሁሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን በተአምኖ ንሴፎ ትንባሌ ዚአከ መዓልተ ወሌሊተ፤ በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡ እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል” ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፴፬፥፯)፡፡ ይህን እንድናደርግም የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡ የቅዱስ ገብርኤል፣ ቅድስት ኢየሉጣ እና ቅዱስ ቂርቆስ ጸሎታቸውና ምልጃቸው ይጠብቀን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ

“ዓላማዬ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችን በዕውቀት ማነጽ ነው” (ሄኖክ ግዛው)

ሄኖክ ግዛው በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የ፳፻፲፯ ዓ.ም ተመራቂ ነው፡፡ በሒሳብ ትምህርት ክፍል አጠቃላይ ውጤት የትምህርት ክፍሉ ሜዳልያና በዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ ውጤት ደግሞ 3.99 በማስመዝገብ በከፍተኛ ውጤት የዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል፡፡ ዩኒቨርሲቲውም በመደበኛ መምህርነት በመቅጥር የሁለተኛ ዲግሪውንም ስፖንሰር በማድረግ እንዲማር ዕደል ሰጥቶታል፡፡

ሄኖክ ይህንን ውጤት እንዴት ማምጣት ቻለ? የቤተሰቦቹና የመምህራኑ ድርሻ ምን ነበር? አስተዳደጉና ለትምህርት የሰጠውን ትኩረት አስመልክተን ከዝግጅት ክፍላችን ጋር ቆይታ አድርጓል፡፡ እንዲህ ተዘጋጅቷል፡፡

ስለ አስተዳደግህ በመግለጽ ውይይታችንን ብንጀምር?

ሄኖክ፡- የተወለድኩት ከወልቂጤ ከተማ 42 ኪሎ ሜትር ርቀት በምትገኘውና ከአበሽጌ ወረዳ ወጣ ብላ በምትገኝ በምዕራብ ሸዋ ዞን ገጠር ቀበሌ ውስጥ ነው፡፡ እንደማንኛውም የገጠር ልጅ ለቤተሰብ እየታዘዝኩ፣ ከብቶች እየጠበቅሁና እያሰማራሁ ነው እስከ ዘጠኝ ዓመቴ ያደግሁት፡፡ ትምህርቴንም በሚመለከት አባቴ እስከ ስምንተኛ ክፍል ተምሮ የነበረ ቢሆንም ቤተሰብን ለመርዳትና ራሱንም ለመቻል ወደ ግብርናው ተሰማርቶና ትዳር ይዞ ኖረ፡፡ ነገር ግን ከፍተኛ ቁጭት ስለነበረው የትምህርት እልሁን በእኛ በልጆቹ መወጣት ይፈልግ ነበር፡፡ በአካባቢያችን ጥሩ ትምህርት ቤት ስላልነበረ ታላቅ ወንድሜን አስቀድሞ ወደ ወደ አበሽጌ ከተማ ልኮ ያስተምረው ስለነበር እኔንም ከወንድሜ ጋር ትምህርቴን እንድከታተል ወደ አበሽጌ ላከኝ፡፡ በየሳምንቱ ዓርብ ለሳምንት የሚሆነን ምግብ ይላክልናል፤ የእኛ ድርሻ መማር ብቻ ነበር፡፡

ለትምህርት የነበረህ ፍላጎትና ውጤትህ ቤተሰቦችህ ላይ ያሳደረው ተጽዕኖ አልነበረም?

ሄኖክ፡- ለታናናሾቼ አርአያ ሆኛለሁ ማለት እችላለሁ፤ እኔን ተከትለው እነርሱም ከፍተኛ የትምህርት ፍቅር አላቸው፡፡ እኔ ደግሞ የታላቅ ወንድሜ ውጤታማነት አግዞኛል፤ እኔም በተፈጥሮ የነገሩኝን ነገር ያለመርሳት፣ በትምህርቴም ክፍል ውስጥ አስተማሪዎቼ ሲያስረዱ የመቀበል አቅም ነበረኝ፡፡ በውጤቴም እስከ መጨረሻው ድረስ የደረጃ ተማሪ ነበርኩ፡፡ ስምንተኛ ክፍልንም 100 ውጤት አምጥቼ ዘጠነኛ ክፍልን ለመማር ወደ ወልቂጤ ከተማ መጣሁ፡፡ ወልቂጤም ብዙ አልተቸገርኩም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ተከታትዬ በጥሩ ውጤት ነው ያለፍኩት፡፡ እናትና አባቴ አንዲት እኅትና አራት ወንድ ልጆችን ነው የወለዱት፡፡ ታላቅ ወንድሜ ከኮሌጅ ተመርቆ አዲስ አባባ ሥራ ላይ ነው፣ እኔ እግዚአብሔር ፈቅዶ ዘንድሮ ተመርቄያለሁ፣ ታናሽ ወንድሜ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሦስተኛ ዓመት አርክቴክቸር ተማሪ ሲሆን ትንሹም በትምህርት ላይ ይገኛል፡፡ አንዲት ታላቅ እኅት ነበረችን እርሷም ትታመም ስለነበር ጸበል በሄደችበት ነው ያረፈችውና ከባድ ኀዘን ነበር በቤታችን ውስጥ የተፈጠረው፡፡

ከቤተሰቦቼ ጋር በጣም የጠበቀ ቅርበት ስለነበረኝ አቅማቸው በፈቀደ መጠን ከማበረታታት ወደኋላ አላሉም፡፡ በተለይ አባታችን ተምራችሁ አንድ ደረጃ ላይ መድረስ አለባችሁ እያለ ስለሚመክረን የቅርብ ክትትሉ አልተለየንም፡፡   

በሰንበት ትምህርት ቤት ስለነበረህ ተሳትፎ ብትገልጽልን? 

ሄኖክ፡- ቤተ ክርስቲያን ከጓደኞቼ ጋር እሄዳለሁ፣ በሰንበት ትምህርት ቤትም በአባልነት ወጣ ገባ ያለ ተሳትፎ ብቻ ነበር የነበረኝ፡፡ እንደ ወጣት ዓለም ስባ እንድታስቀረኝ ዕድሉን አልሰጠኋትም፤ እምነቴን ለመጠበቅ ጥረት እያደረግሁ ነው ያደግሁት፡፡ መውደቅ መነሣቱ ቢኖርም በእምነት ጸንቼ ለመኖር የምችለውን ሁሉ ሳደርግ ነበር፡፡ ወደ አገልግሎት የመግባት ዕድሉን ግን አላገኘሁም፡፡ በተፈጥሮ ዝምታን ስለማበዛ ራሴን ለመማር እንጂ ለማገልገል አላዘጋጀሁትም፡፡  

ከፍተኛ ትምህርት ተቋም (ዩኒቨርሲቲ) ስትገባ መንፈሳዊ ሕይወትህን እንዴት ትመራ ነበር?

ሄኖክ፡- በግቢ ጉባኤ ውስጥ በአባልነት ስሳተፍ ነበር፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ መጸለይ አዘወትራለሁ፡፡ አገልግሎትን በተመለከተ ግን ኮርስ መከታተልና በልዩ ዝግጅት ከመሳተፍ ውጪ ወደ አገልግሎት አልገባሁም፡፡

ቤተሰብ ውጤታማ ሆነህ እንድትወጣ ከመጓጓትና ለትምህርትህ ልዩ ትኩረት እንድትሰጥ ከመፈለግ አንጻር ወደ ግቢ ጉባኤ እንዳትሄድ አልተከለከልክም?

ሄኖክ፡- ቤተሰቦቼ ለትምህርት ልዩ ትኩረት እንደምሰጥ ስለሚያውቁ ወደ ቤተ ክርስቲንና ግቢ ጉባኤ እንዳልገባ ያደረጉት ጫና አልነበረም፡፡ እኔም ይህንን ስለምረዳ መቼ ቤተ ክርስቲያን መሄድ፣ መቼ ግቢ ጉባኤ መሄድ እንዳለብኝ ስለማውቅ ሁሉንም አጣጥሜ ለመጓዝ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡

የትምህርት ክፍሌ (የሒሳብ ትምህርት) ልዩ ትኩረት የሚሻ የትምህርት ዓይነት በመሆኑ ከመምህራን ከማገኘው ዕውቀት በተጨማሪ በራሴም ከፍተኛ ጥረት ሳደርግ ነበር፡፡ የመምህራኖቼም ጥሩ ድጋፍና አይዞህ ባይነት አልተለየኝም ነበር፡፡    

የውጤታማነትህ ምሥጢር ምንድነው?

ሄኖክ፡- የመጀመሪያው ውሳኔ ነው፡፡ በዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ ከተሰጡት 50 የትምህርት ዓይነቶች 43A+ ነውያመጣሁት፣ ከአንድ ትምህርት A-ውጪቀሪዎቹ A ነው ያስመዘገብኩት፡፡ማንኛውም ቤተሰብ ልጆቹ ተምረው ዶክተር እንዲሆኑ ነው የሚመኘው፡፡ ልጆችም ብንሆን ከልጅነት ጀምሮ ዶክተር ወይም አውሮፕላን አብራሪ እንድንሆን እንመኛለን፡፡ እኔ ግን መምህርነትን ከልጅነቴ ጀምሮ ነው ስመኘው የኖርኩት፤ ቤተሰብም ሲጠይቀኝ መምህር ነው የምሆነው ስለምላቸው በውሳኔዬ ነው የጸናሁት፡፡ የመጀመሪያ ዓመት ውጤቴም ከፍተኛ ስለነበረ ለምን ሕክምና አታጠናም የሚሉኝ ብዙዎች ነበሩ፡፡ እኔ ግን ፍላጎቴ ስላልነበር ተማሪዎች የትምህርት ክፍላቸውን ሲመርጡ እኔ ግን ሐሳቤን እንዳልቀይር ግቢውን ትቼ በመውጣት ወደ ቤተ ክርስቲያን ነው የሄድኩት፡፡ 

ከግቢው ከፍተኛ ውጤት ማምጣት አለብኝ ብዬ አልነበረም የማጠናው፡፡ ነገር ግን በሂደት ጥሩ ውጤት እያመጣሁ መሆኔን ስረዳ ነው በጥሩ ውጤት ተመርቆ የመውጣት ፍላጎቴ ከፍ ያለውና ቢያንስ ሜዳልያ ማግኘት አለብኝ የሚለው ፍላጎት ያደረብኝ፡፡ የጓደኛ ግፊት፣ ሌሎች ሱሶች የሚያጠቁኝ ሰው አይደለሁም፤ ከዓላማዬ የሚያዘናጋኝም የተለየ ችግር ስላልነበር ሙሉ ትኩረቴን ትምህርቴ ላይ ነበር የማሳርፈው፡፡ 

ፈተና ሲኖርም ጠለቅ ያለ ጥናቴን በሦስት ቀን ውስጥ አጠናቅቃለሁ፤ ክፍል ውስጥ የሚሰጠውን ትምህርት በትኩረት እከታተላለሁ፤ አንድ ጊዜ ከተረዳሁ ደግሞ አልረሳም፣ በዚህ ላይ የሒሳብ ትምህርት ክፍል መምህራኖቼ ድጋፍ ስለማይለየኝ በውጤት መዋዠቅ ውስጥ ሳልገባ እስከ መጨረሻው መዝለቅ ችያለሁ፡፡ 

ለጥናት የትኛውን ጊዜ ትመርጥ ነበር?

ሄኖክ፡- ከሰኞ እስከ ዓርብ ጠዋትና ከሰዓት በኋላ ትምህርት ስለሚኖረን ለጥናት ያለኝ ጊዜ ማታ ነው፡፡ ስለዚህ ከራት በኋላ ያለውን ጊዜ ነው የምጠቀመው፡፡ ራት ከበላሁ በኋላ ቢበዛ እስከ ሌሊቱ ሰባትና ስምንት ሰዓት እያጠናሁ ልቆይ እችላለሁ፡፡ ይህ ሰዓት ለእኔ ልዩ ምቾት የሚሰጠኝ ጊዜ ነው፡፡  

ጊዜህን ለትምህርትህ እንደሰጠህ ሁሉ በትርፍ ሰዓትህ በምን ትዝናና ነበር?

ሄኖክ፡- ትርፍ ሰዓት ሲኖረኝ ቀድሞ ሙዚቃ ነበር የማደምጠው ግቢ ከገባሁ በኋላ ግን ከቀድሞ ይልቅ ይበልጥ ቤተ ክርስቲያንን እያወቅኋት በመምጣቴ መዝሙር በመስማት፣ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ነው የማሳልፈው፡፡

በትምህርትህ ውጤታማ እንድትሆን የቤተሰብ ድጋፍ እንዴት ነበር?

ሄኖክ፡- ቤተሰቦቼ በመካከለኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ ናቸው፡፡ ገንዘብም ቢሆን የሚያስፈልገኝን ሁሉ በማሟላት ሲደጉሙኝ ቆይተዋል፡፡ አባቴ ለትምህርት ከተባለ ያለምንም ቅሬታ የቻለውን መሥዋዕትነት ይከፍላል፣ የጠየቅነውን ሳያሟላ ዕረፍት አይኖረውም፡፡ ስለዚህ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ውስጥ ሆኜ ቤተሰቦቼ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ አላሉም፡፡ እኔም አደራቸውን ለመወጣት የቻልኩትን ሁሉ ለማድረግ ጥረት አድርጌያለሁ፡፡   

አባቴ ለትምህርት ያለው ፍቅር ከፍተኛ ስለሆነና እርሱ ያጣውን በልጆቹ መበቀል ስለሚፈልግ “ከእኔ ምንም አትጠብቁ፣ የማወርሳችሁም ነገር የለኝም፤ ስለዚህ ጠንክራችሁ ተማሩ” በማለት ከፍተኛ ግፊት ስለሚያደርግ ለትምህርት ከሆነ ማንኛውንም መሥዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ የሆነ ቆራጥ አባት ነበር፡፡ ወላጅ እናቴም ከአባቴ የተለየ አመለካከት አልነበራትም፡፡ ለራሳቸው እያስፈለጋቸው አጉድለው ለእኛ ለልጆቻቸው የሚያደረጉት ነገር ያስገርመኛል፡፡ ሁል ጊዜም ከራሳቸው ይልቅ እኛን ያስቀድማሉ፡፡ እዚህ ደረጃ ላይ ለመድረሴ የወላጆቼ ክትትልና ድጋፍ ከፍተኛ ድርሻ ነበረው፡፡

በግቢ ቆይታህ ከጓደኞችህ ጋር ምን ዓይነት ግንኙነት ነበረህ?

ሄኖክ፡- እኔ ጓደኛ ከማያበዙት ወገን ነኝ፡፡ በማደሪያ ክፍላችን ውስጥ አብረን ስላለን አንዳንድ ነገሮችን ልንነጋገር፣ ልንደጋገፍ እንችላለን፡፡ ያ ግንኙነት ጓደኝነት ነው ማለት አይደለም፡፡ ክፍል ውስጥም እንዲሁ፡፡ ነገር ግን ትምህርቴን ጨርሼ ከግቢ እስክወጣ ድረስ አንድ ጓደኛ ብቻ ነበረኝ፡፡ ከእርሱም ጋር ትርፍ ሰዓት ካለን ነው የምንገናኘው፤ በተለይ ቅዳሜ ከቅዳሴ በኋላ ጊዜ ስለሚኖረን አብረን እንሆናለን፣ ሻይ ቡና እንላለን፡፡ በግል ሕይወታችን ዙሪያም እንመካከራለን፡፡ በተረፈ ቀሪውን ሰዓት ደግሞ ዕረፍት አደርጋለሁ፡፡

ከክፍል ልጆች ጋር ደግሞ ፈተና ከመድረሱ በፊት አስረዳን ስለሚሉኝ ባዶ ክፍል ፈልገን አስረዳቸዋለሁ፣ እኔም እያስረዳሁ አብሬ እማር ነበር ማለት እችላለሁ፡፡

በግቢ የነበረህ ቆይታ በድል ተወጥተኸዋልና የወደፊት ዓላማህ ምንድነው?

ሄኖክ፡- ተቋሙ የመምህርነት ዕድሉን ሰጥቶኛል፣ በዚህ ላይ ደግሞ ሁለተኛ ዲግሪዬን እንድማር ስፖንሰር ሆኖኛል፡፡ የወደፊት ዕቅዴ በመምህርነቱ የመቀጠል ፍላጎት ቢኖረኝም ግቢ ውስጥ ለረጅም ጊዜ የመቆየት ፍላጎት የለኝም፡፡ ከታች ወርጄ አንደኛ ወይም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ ለማስተማር ነው የማስበው፡፡ ዓላማዬ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎችን በዕውቀት ማናጽ ነው፤የትምህርት መሠረት የሚገነባው ከሕፃንነት ጀምሮ ነውና ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ የድርሻዬን መወጣት አለብኝ፡፡ በማኅበረሰብ አገልግሎትም የመሳተፍ ፍላጎት ስላለኝ ይህንን ሕልሜን ለማሳካት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ ልጆቹን መንገድ ማሳየት፣ መምራት ላይ ትኩረት አደርጋለሁ፡፡ እዚሁ ወልቂጤ እያስተማርኩም ታናናሽ ሁለቱን ወንድሞቼን ማስተማር፣ አብሬአቸው መኖርና ውጤታማ ይሆኑ ዘንድ መርዳት እንዳለብኝ ራሴን አሳምኜዋለሁ፡፡

በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እና በመንፈሳዊ ሕይወት ጸንቶ ለመኖር የምታደርገው ጥረት ምን ይመስላል?

ሄኖክ፡- ከልጅነቴ ጀምሮ ከተሳታፊነት ባለፈ ደፍሮ ወደ አገልግሎት የመግባት ልምዱ የለኝም፡፡ ጸጋውም ያለኝ አይመስለኝም፡፡ ነገር ግን ያለ መንፈሳዊ ሕይወት ትርጉም አይኖረውምና ጥሩ ክርስቲያን መሆን፣ ቤተሰቤንም የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ተገንዝበው በመልካም መንገድ ላይ እንዲጓዙ አርአያ መሆን እፈልጋለሁ፡፡

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ ተማሪዎች በመደበኛ ትምህርታቸውም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ ከተሞክሮህ በመነሣት ልምድህን ብታካፍል?

ሄኖክ፡- የገጠር ወይም የከተማ ልጅ ብሎ መከፋፈሉ አስፈላጊ ባይሆንም እስከሚለምዱት ድረስ ጫናው በገጠር ልጆች ላይ የሚበረታ ይመስለኛል፡፡ እኔም የተገኘሁት ከገጠር ስለሆነ ስሜታቸውን እጋራለሁ፡፡ ማንኛውም ተማሪ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሲገባ ግር ሊለው ይችላል፡፡ የመደናገጥ፣ ፍርሃት ውስጥ የመግባት ችግር ሊገጥመው ይችላል፡፡ ነገር ግን ይህንን በመቋቋም ከማንም እንደማያንስና የተሻለ ብቃት እንዳለው በማመን ተስፋ ሳይቆርጥ መማር ይገባዋል፡፡

ትምህርት ጊዜን ይፈልጋል፣ ለፈተና ብቻ ብለን የምናጠናው ሳይሆን ዕውቀታችን ለማስፋት፣ ወደፊት ለሚጠብቀን የሕይወት ምዕራፍ እንደሚረዳን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ከማኅበራዊ ሚዲያ ጋር ያላቸውን ቁርኝት መቀነስ፣ ሞባይላቸውን ለትምህርት አጋዥ ለሚሆኑ አገልግሎቶች ብቻ ማዋል ይጠበቅባቸዋል፡፡ ማኅበራዊ ሚዲያው ብዙዎችን ከዓላማቸው እያዘናጋ ያሰቡበት እንዳይደርሱ እንቅፋት ስለሚሆን ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ተሞክሮህን ስላካፈልከን በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ሄኖክ፡- እኔም አመሰግናለሁ፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ማስታወቂያ

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ አገልግሎቱን በማጠናከር በግቢ ጉባኤያት ላይ ውጤታማ ሥራ ለመሥራትና ብቁ አገልጋዮችን ለማፍራት ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ ፕሮጀክቶቹን ለማስፈጸም ይረዳውም ዘንድ ልዩ የገቢ ማሰባሰቢያ ትኬት ሽያጭ ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በማሠራጨት ላይ ይገኛል፡፡ እርስዎም ትኬቱን በመግዛት ትውልድን ለመቅረጽ በሚደረገው ጥረት ውስጥ አሻራዎን ያኑሩ፡፡

ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወቅዱስ ጳውሎስ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርታ የሚነበበውን ምንባብ፣ የሚዘመን ዜማ በቀለም ለይታ ሐምሌ ፭ ቀን ከዋዜማው ጀምሮ በታላቅ ድምቀት በዓላቸውን ከምታከብላቸው ሐዋርያት መካከል የሊቀ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ ዕረፍት አንዱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በምድር ላይ ሳሉ እግዚአብሔርን አምነው፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ቃል አስገዝተው ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ድውያንን እየፈወሱ፣ በየደረሱበት ቃለ እግዚአብሔርን ለተራቡና ለተጠሙ ምእመናን በመመገብና በማጠጣት በሚታወቁ ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን የተከበበች ናት፡፡ ታሪካቸውንም ሰንዳ ለትውልድ በማስተላለፍ ብቸኛዋ ተቋም ናት፡፡ 

የሐዋርያትን ታሪክ ለማወቅ ዋናው ምንጩ የቤተ ክርስቲያን የታሪክ መጻሕፍት ናቸው። በዚህም መሠረት በቤተ ክርስቲያናችን ሐምሌ ፭ ቀን በዓላቸውን ከምታከብርላቸው ሐዋርያት መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ታሪክ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በገሊላ ቤተ ሳይዳ ሲሆን እናቱ ባወጣችለት ስም ስምኦን እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ በጐልማሳነቱ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ተሠማራ። በ፶፭ ዓመት ዕድሜውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዝሙርነት ጠርቶታል፡፡ “በገሊላ ባሕር ዳር ሲመላለስም ሁለቱን ወንድማማቾች ጴጥሮስንና እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ዓሣ አጥማጆች ነበሩና ጌታችን ኢየሱስም ‘ኑ ተከተሉኝ፤ ሰውን የምታጠምዱ እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፬፥፲፰-፳) መረባቸውንም ትተው ተከተሉት፡፡ ቅዱስ ጰጥሮስ በዚህ መንገድ ነው የተጠራውና ቤተሰቡንና ያለውን ሁሉ ትቶ ጌታችንን የተከተለው፡፡

በቂሳርያ ከተማ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን “እናንተስማን ትሉኛላችሁ? ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ ብፁዕ ነህ፤ በሰማይ ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና፡፡ እኔም እልሃለሁ፡- አንተ ዐለት ነህ፤ በዚያች ዐለት ላይም ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲዖል በሮች አይበረቱባትም” አለው፡፡ ጴጥሮስ የሚለው ስም በላቲን ቋንቋ ዐለት ማለት ነው፤ በአርማይክ ደግሞ ኬፋ ይባላል። (ማቴ. ፲፮፥፲፮) በዐለት ላይ የተመሠረተ ቤት ንፋስ በነፈሰ ጊዜ እንደማይፈርስ ሁሉ በክርስቶስ የተመሠረተችው ቤተ ክርስቲያንም በንፋስ የተመሰለው ዲያብሎስ ዙሪዋን ቢዞርም ለያጠፋት እንደማይችል ያመለክታል፡፡ 

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥብርያዶስ ባሕር ላይ በእግሩ ሲራመድ ተመልክቶ እርሱም ይሄድ ዘንድ ፈቃድ የጠየቀ፣ መሄድ የጀመረና ማዕበሉን ፈርቶም የተጠራጠረ፣ በዚህም ምክንያት ለመስጠም የደረሰ፣ ጌታችንን ያድነው ዘንድ የተማጸነ፣ ጌታችንም በጥያቄው መሠረት ከመስጠም ያዳነው እንደሆነ ቅዱስ ወንጌል ያስተምረናል፡፡ (ማቴ. ፲፬፥፳፪-፴፫)

በቅፍርናሆም ጉባኤ ጌታን ምሥጢረ ቁርባንን ሲያስተምር አይሁድ ስላልገባቸው ወደ ኋላ አፈገፈጉ። “እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላችሁ?” ብሎ ጌታችን ሐዋርያትን ጠየቃቸው። “ጌታ ሆይ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም የሕይወት ቃል አለህ። እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ እናምናለን” በማለት ሐዋርያትን ወክሎ የመለሰ እርሱ ነው። (ዮሐ. ፮፥፷፮-፷፰)

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እረኛው መሞትና ስለ በጎቹ መበተን ሲያስተምር ለደቀ መዛሙርቱ “በዚህች ሌሊት ሁላችሁም ትክኛላችሁ” ብሎ በተናገረ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ “ሁሉም ቢክዱህ እንኳ እኔ ከቶ አልክድህም” (ማቴ. ፳፮፥፴፬) ብሎ ተናግሯል፡፡ ነገር ግን በዚያው ሌሊት ጌታችን በአይሁድ በምቀኝነት ይሰቅሉት ዘንድ በተያዘ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አስቀድሞ የተናገረውን ቃል ዘንግቶ ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ ክዶታል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ የሚታወቅበት ሌላው ትልቁ ነገር ንስሓው ነው። አምላኩን መበደሉን ሲረዳ ተጸጽቶ ምርር ብሎ የንስሓ ዕንባን አንብቷል፡፡ 

በበዓለ ሃምሳ ለደቀ መዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ ለተሰበሰቡት አይሁድ ወንጌልን የሰበከ፣ ሦስት ሺህ ምእመናንን አሳምኖ የመጀመሪያዋን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የመሠረተ እርሱ ነው። (የሐዋ. ፩፥፲፮-፳፫ ፤ ፪፥፲፬-፴) ልዑል እግዚአብሔር ባደለው ጸጋ ጥላው እንኳን ድውያንን ይፈውስ ነበር። (ሐዋ.  ፭፥፲፭)።

ቅዱስ ጴጥሮስ  በፍልስጥኤም፣  በሶርያ፣  በጳንጦን፣  በገላትያ፣  በቀጰዶቅያ፣ በቢታንያ እና በሮሜ ሰብኳል። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በሮሜ አንድ ዓመት ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ካስተማረ በኋላ የሮሜ ክርስቲያኖች እየበዙ ከመምጣታቸውም በላይ የክርስትናው ጉዞ እስከ ሮማ ባለሥልጣናት ደረሰ። የኔሮን የቅርብ ባለሥልጣናት የሆኑት የአልቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች ወደ ክርስትናው ገቡ። በዚህን ጊዜ ኔሮን ንጉሠ ሮማ በቅንዓት ተነሣባቸው።

ኔሮን በሮም የነገሠው በ፶፬ ዓ.ም. ነው። በመንግሥቱ መጀመሪያ ደግ ሰው ነበረ። ነገር ግን በነገሠ በዓመቱ የጨካኝነት ዐመሉ ብቅ ማለት ጀመረ እና የአባቱን ልጅ አስገደለ። በ፶፱ ዓ.ም. ደግሞ እናቱን በመርዝ ገደለ። በ፷፫ ዓ.ም. እያስተማረ ያሰደገውን መምህሩን ፣ በ፷፪ ዓ.ም. የልጅነት ሚስቱን አግታሺያን አስገደለ። ከእርስዋ በኋላ ያገባትን ሚስቱንም ፓፒያን ገደላት። በ፷፬ ዓ.ም ከከተማው ወጣ ብሎ በሚገኘው ቤተ መንግሥቱ ተቀምጦ የሮማን ከተማ እሳት ለቀቀባት። የሮም ሕዝብ በደረሰው አደጋ እጅጉን ተቆጣ። ኔሮንም በክርስቲያኖች አመካኘ። በዚህም የተነሣ በሮማ ከተማ ሁለት ዓይነት ወሬ መናፈስ ጀመረ።

የሮማ አማልክት በክርስቲያኖች ሃይማኖት ስለተቆጡ በከተማዋ እሳት አዘነቡባት የሚለው የመጀመሪያው ሲሆን ክርስቲያኖች ሆን ብለው ከተማዋን አቃጥለዋታል የሚለው ደግሞ ሁለተኛው ወሬ ነበር። የከተማው መጋየት ያበሳጨው የሮማ ሕዝብ፣ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ እያወጣ መግደሉን ተያያዘው። ይህን የሰሙት የአግቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች (የሮም ባለሟሎች ነበሩ) “አንተ ትረፍልን” ብለው በከተማዋ ግንብ በገመድ አሥረው በቅርጫት በማውረድ ቅጥረ ሮማን ለቅቆ እንዲወጣ አደረጉት።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በኦፒየም ጎዳና ጉዞውን ቀጠለ። ሮማን ለቀቀ። እያዘገመ በሸመገለ ጉልበቱ ሲጓዝ አንድ ቀይ ጐልማሳ ወደ እርሱ ሲመጣ አየ። እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን መሆኑን ተረዳ። ወዲያው በፊቱ ተደፋና “ጌታዬ ወዴት እየተጓዝክ ነው?” አለና ጠየቀው። “ዳግም በሮም ልሰቀል” አለው። በዚህ ሰዓት ቅዱስ ጴጥሮስ አዘነና እንደገና ወደ ሮም ተመለሰ። የኔሮን ወታደሮች እየፈለጉት ነበር። “እነሆኝ ስቀሉኝ” አለ ቅዱስ ጴጥሮስ። ያን ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስን ይዘው አሠሩት። ከጥቂት ቀናት በኋላም ሮማውያን የመስቀያውን እንጨት አቀረቡለት። ያን ጊዜ “እኔ እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም” በማለት ቁልቁል እንዲሰቅሉት ለመነ። እንደለመነውም ሐምሌ ፭ ቀን ፷፯ ዓ.ም ቁልቁል ሰቅለውት በሰማዕትነት ዐረፈ።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዘሩ ከዕብራዊያን፣ ከብንያም ነገድ ሲሆን የተወለደውም በጠርሴስ ከተማ ነው። ጠርሴስ በንግድዋ የታወቀች የኪልቂያ ዋና ከተማ ናት። በከተማዋ እስከ አምስት መቶ ሺህ የሚገመቱ ከየሀገሩ የተሰባሰቡ ሕዝቦች ነበሩባት። ሮማውያን በሥራቸው ለሚተዳደሩት ሕዝቦች ሮማዊ ዜግነትን ይሰጡ ስለነበር፥ የቅዱስ ጳውሎስ አባት በዜግነት ሮማዊ ነበር። ይህም ለቅዱስ ጳውሎስ ተላልፎለታል።

ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ከታወቀው የገማልያል ትምህርት ቤት ገባ። በዚያም የአይሁድን ሕግና ሥርዓት እየተማረ እስከ ፴ ዓመቱ ቆየ። በ፴ ዓመቱ የአይሁድ ሸንጎ አባል ሆኖ ተቆጠረ።ለኦሪታዊ እምነቱም ቀናተኛ በመሆኑ ክርስቲያኖችን ያሳድድ ነበር። ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ ተከሶ በአይሁድ ሸንጎ ፊት በቀረበ ጊዜ በድንጋይ ተወግሮ በሰማዕትነት ሲያርፍ የወጋሪዎችን ልብስ በመጠበቅ የተባበረ ነው። “ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስን በገደሉትም ጊዜ እኔ እዚያ አብረአቸው ነበርሁ፤ የገዳዮችንም ልብስ እጠብቅ ነበር” እንዲል፡፡ (ሐዋ. ፳፪፥፳)

ቅዱስ ጳውሎስ በደማስቆ ከተማ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን ሲሰማ ወደ ሊቀ ካህናቱ ቀርቦ ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የሚያስችለውን የፈቃድ ደብዳቤ አገኘ። ከዚህም በኋላ ጭፍሮችን አስከትሎ ወደ ደማስቆ አመራ። ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ከተማዋ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ነበር ከሰማይ የወረደው ብርሃን አካባቢውን ያለበሰውና “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚለውን ድምፅ የሰማው። ሐዋርያው ጳውሎስም “ጌታ ሆይ ማን ነህ?” ብሎ ጠየቀ። “አንተ የምታሳድደኝ እኔ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ። የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል” ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናገረው። ያን ጊዜም በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ “ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?” ሲል ጠየቀ። ከዚህ በኋላ ተነሥቶ ወደ ደማስቆ እንዲገባ ተነገረው። ነገር ግን ዓይኖቹ ማየት አልቻሉም፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ ሐናንያ ወደሚባል ሰው ወሰዱት፡፡ ሐናንያም እጁን ጭኖ ጸለየ፡፡ ከዓይኖቹም እንደ ቅርፊት ያለ ነገር ተገፎ ወደቀለት፣ ዓይኖቹም ተገለጡ፣ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ ስለ ጌታችንም “የእግዚአብሔር ልጅ ነው” በማለት መስበኩን ቀጠለ፡፡ (የሐዋ. ፱፥፩-፲፰)

አይሁድም ቅዱስ ጳውሎስን ይገድሉት ተነሡ። ሐዋርያት ግን የቅዱስ ጳውሎስን መመለስ ለማመን ቢቸገሩም በርናባስ ወስዶ የጳውሎስን መመለስ በመተረክ እንዲያምኑት አደረጋቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጠርሴስ ከተማ ለዘጠኝ ዓመታት ቆይቷል። ከኢየሩሳሌም ውጭ የአሕዛብ ከተማ በነበረችው በአንጾኪያ የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፋ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመጀመሪያው ጉዞ ያደረገው ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ጥሪ በአሕዛብ ሀገር ወንጌልን ለመስበክ ከበርናባስ ጋር ወጡ። በዚህ ጉዞአቸው በጠቅላላው ወደ ሁለት ሺህ ኪሎ ሜትር የሚደርስ መንገድ በእግር ተጉዟል። ይህም ጉዞ የተከናወነው በ፵፮ ዓ.ም. አካባቢ ነው። የተሸፈኑትም ሀገሮች ሲሊንውቂያ፣ ቆጵሮስ፣ ስልማን፣ ጳፋ፣ ጰርጌን፣ ገላትያ፣ ጵስድያ፣ ኢቆንዮን፣ ሊቃኦንያ፣ ልስጥራ፣ደርቤን፣ጵንፍልያ፣አታልያና አንጾኪያ ናቸው።

ሁለተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶ ዓ.ም. ገደማ ነው። በመጀመሪያው ጉዞ ማርቆስ አብሮ ተጉዞ ነበር። ነገር ግን ጵንፍልያ ከተማ ሲደርስ እናቱ ስለናፈቀችው መመለስ በመፈለጉ በርናባስ ወደ ኢየሩሳሌም ይዞት መጣ። ስለዚህም በሁለተኛው ጉዞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲላስን ይዞ ወደ ኪልቂያ ሶርያ ሲጓዝ በርናባስ ደግሞ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ ሄደ። በዚህ ጉዞው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ግሪክ ደርሶአል። የተጓዘባቸውና ያስተማረባቸው ከተሞችም፦ ደርብያ፣ ልስጥራ፣ፍርግያ፣ ገላትያ፣ ሚስያ፣ጢሮአዳ፣ ሳሞትራቄ፣ ናፑሊ፣ ፊልጵስዩስ፣ ተሰሎንቄ፣ በርያ፣አቴና፣ ቆሮንቶስ፣ አንክራኦስ፣ አፌሶን፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌምና አንጾኪያ ናቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ያገኘው በዚሁ ጉዞው በልስጥራ ከተማ ነው።

ሦስተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶፬ ዓ.ም. ሲሆን የተሸፈኑትም ሀገሮች የሚከተሉት ነበሩ። ገላትያ፣ ፍርግያ፣ ኤፌሶን፣ መቄዶንያ፣ ፊልጵስዩስ፣ ቆሮንቶስ፣ ጢሮአዳ፣ አሶን፣ ሚልጢኒን፣ አንጠቀከስዩ፣ ትሮጊሊዩም፣ መስጡ፣ ቆስ፣ ሩድ፣ ጳጥራ፣ ጢሮስ፣ ጵቶልማይስ፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም ናቸው።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከልዩ ልዩ ሀገሮች ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ዕርዳታ ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን በመያዝ ሦስተኛውን ጉዞ አጠናቅቆ ኢየሩሳሌም ገባ። ነገር ግን ኢየሩሳሌም የገባበት ጊዜ የፋሲካ በዓል ስለነበር ከልዩ ልዩ ሀገሮች የተሰበሰቡ አይሁድ በከተማዋ ነበሩ። እነዚህ በዝርወት የሚኖሩ አይሁድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በየሀገራቸው በትምህርቱ የተነሣ ሲቃወሙት የነበሩ ናቸው።

መስበኩን በመቀጠሉ ምክንያት በ፶፰ ዓ.ም በሮም ለቁም እሥር ተዳረገ። የሁለቱን ዓመት የቁም እሥር እንደጨረሰ ወደ ኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ። ይህም በ፷ዎቹ ዓ.ም ነው። በፍርድ ቤቱ በተደረገው ምርመራ የሮሜን ሕግ የሚቃወም ምንም ወንጀል ስላልተገኘበት በነፃ ተለቀቀ፤ ከዚህ በኋላ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አራተኛውንና የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያልመዘገበውን ጉዞውን ያደረገው። ይህ ጉዞው በመታሠሩ አዝነው ተክዘው የነበሩ ክርስቲያኖችን ለማጽናናት የጀመራቸውን ሥራዎች ፍጻሜ ለማየት የተደረገ ጉዞ ነው። በዚህም ጉዞው ኢየሩሳሌምን፣ ኤፌሶንን፣ ሎዶቅያን፣ መቄዶንያን፣ ቀርጤስን፣ ጢሮአዳን፣ ድልማጥያን፣ እልዋሪቆን፣ ኒቆጵልዮን፣ ብረንዲስን፣ ጎብኝቷል። በዚህ የመጨረሻ የስብከት ጉዞው ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል።

በመጨረሻ በ፷፬ ዓ.ም. ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ምን እንደምትመስል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት። የሮም ሕዝብ በከተማው መቃጠል በማዘኑና በማመፁ ነገሩን ሁሉ በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ። በዚህም የተነሣ ክርስቲያን የተባለ ሁሉ መሰደድ፣ መሠየፍ፣ መታረድ እጣ ፈንታው ሆነ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኒቆጵልዮን ከተማ ሲያስተምር በ፷፭ ዓ.ም. ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ። ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታሥሮ ከቆየ በኋላ በ፸፬ ዓመት ዕድሜው በሮም ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሰይፎ በ፷፯ ዓ.ም. ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት፣ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ዐስራ አራት መልእክታትን ጽፈዋል። የቅዱሳኑ ሐዋርያት ረድኤትና በረከታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፤ አሜን።

ምንጭ፦ መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ ፭፤ መጽሐፍ ቅዱስ ሐዲስ ኪዳን፣

           ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ ቁጥር ፩፤ በማኅበረ ቅዱሳን

ማኅበረ ቅዱሳን የድጋፍ ማሰባሰቢያ የዕጣ ትኬት ማዘጋጀቱ ተገለጸ

ማኅበረ ቅዱሳን የተቋማዊ ለውጥ ትግበራን ተግባራዊ በማድረግ አገልግሎቱን እያከናወነ የሚገኝ ሲሆን ይህን ተከትሎ በተከለሰው የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት መሠረት በግቢ ጉባኤያት (በዩኒቨርሲቲዎች እና ኮሌጆች) ለሚማሩ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች በሃይማኖት እና በሥነ ምግባር አንጾ ለማውጣት ለሚተገብራቸው የመምህራን ማፍራት፣ የመመማሪያ መጻሕፍት ዝግጅት፣ እንዲሁም የቨርቹዋል ሥልጠና ማእከል ማቋቋሚያ የሚውል የድጋፍ ማሰባበሰቢያ የዕጣ ትኬት አዘጋጅቷል፡፡ የዕጣ ትኬቱንም ከሐምሌ 01 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሥርጭት እና ሽያጭ መጀመሩን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ አበበ በዳዳ ገልጸዋል፡፡

የዕጣ ትኬቱም ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና ቤተሰቦቻቸው፣ ለማኅበሩ አባላት እና ቤተሰቦቻቸው እንዲሁም ለሌሎች ደጋፊ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን የቀረበ ሲሆን የአንድ ትኬት ዕጣ ዋጋ 100 (አንድ መቶ ብር) ብር መሆኑን አቶ አበበ ገልጸዋል፡፡

የዕጣ ትኬቱም ልዩ ልዩ ሽልማቶችን ያካተተ ሆኖ ተዘጋጅቷል፡፡ ከሽልማቶቹ መካከል፡-

  • ለሰባት ቀናት ወደ ቅድስት ሀገር የኢየሩሳሌም ጉዞ (ጉብኝት)፣
  • ለሰባት ቀናት ወደ ግብጽ ገዳማት ጉዞ (ጉብኝት)፣
  • ለአምስት ቀናት ከአንድ ቤተሰብ ጋር (በአውሮፕላን) ከኢትዮጵያ ገዳማት ወደ አንዱ መንፈሳዊ ጉብኝት እና ሌሎችንም ልዩ ልዩ ዕጣዎችን አካትቷል፡፡

ትኬቱን ከግቢ ጉባኤ ተማሪዎች፣ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት እንዲሁም በማኅበሩ የልማት ተቋማት ሱቆች ማግኘት ትችላላችሁ፡፡

ዕጣው የሚወጣበት ቀን ኅዳር 21 ቀን 2018 ዓ.ም ነው፡፡

ዘገባው፡- የማኅበረ ቅዱሳን ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ነው፡፡ 

በደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና የወሰዱ ሠልጣኞች ተመረቁ

በማኅበረ ቅዱሳን የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በሥሩ ለሚገኙና ከተለያዩ ግቢ ጉባኤያት ለተወጣጡ ፸፮ አገልጋዮች የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና በመስጠት አስመረቀ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩትን አባላት አቅም ለመገንባትና የማኅበሩን እንዲሁም የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በሚገባ የተረዱ፤ መንፈሳዊ ሕይወታቸውም የተስተካከለና አርአያ ሆነው ግቢ ጉባኤን ሊመሩ የሚችሉ የአመራር አባላትን ለማፍራት ታስቦ በክረምት ወቅት በተለያዩ ማስተባበሪያዎች ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት በሐዋሳ እና በወላይታ ሶዶ የሥልጠና ማእከላት የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ በሐዋሳ የሥልጠና ማእከል ከሐዋሳ፣ ከባሌ ሮቤ፣ ከሻሸመኔ፣ ከዲላ ማእከላትና ከቡሌ ሆራ ልዩ ወረዳ ማእከል ከሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ውስጥ ለተመለመሉ ፳፮ አገልጋዮች የደረጃ ሁለት የተተኪ አመራርነት ሥልጠና ከሰኔ ፩ እስከ ሰኔ ፯ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም. ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ሥልጠናዎቹም፡-  

  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመሪነት ሚና ትናንት፣ ዛሬ እና ነገ
  • ኦርቶዶክሳዊነት ሕይወቱና ክህሎቱ
  • የአኀት አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ
  • ዓለማዊነት (Secularism) ከኦርቶዶክስ እሳቤና ኑሮ አንጻር
  • ማኅበረ ቅዱሳን ማነው?

በሚሉና ሌሎችም ርእሰ ጉዳዮች ላይ ልምድ ባላቸው መምህራን የተሰጠ ሲሆን ከሥልጠናውና ከአሠልጣኖቹ የሕይወት ተሞክሮና ልምድ ዕውቀት እንዳገኙም ሠልጣኞቹ አስረድተዋል፡፡ በሥልጠናውም ሦስት እኅቶችና ፳፫ ወንዶች ተሳትፈው ሰኔ ፯ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ተጠናቋል፡፡

በተመሳሳይ በወላይታ ሶዶ ማእከል በርእሰ አድባራት ወገዳማት ደብረ መንክራት አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ከአርባ ምንጭ፣ ከወላይታ ሶዶ፣ ከጂንካ፣ ከሆሳዕና እና ከዱራሜ ማእከላት ስር ከሚገኙ ግቢ ጉባኤያት የተመለመሉ ፴፰ ወንዶችና ፲፪ እኅቶች በድምሩ ፶ ሠልጣኞች ከሰኔ ፰ እስከ ፲፬ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም የደረጃ ሁለት አመራርነት ሥልጠና ወስደው ተመርቀዋል፡፡

የደረጃ ሁለት የአመራርነት ሥልጠናው በሐዋሳ ማእከል ከተሰጠው ሥልጠና ጋር ተመሳሳይ ርእሰ ጉዳዮችን ያካተተ ሲሆን በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክትም የተካሄደው ሥልጠና እጅግ ጠቃሚ የሆነና ሊበረታታ የሚገባ መሆኑን ጠቅሰው ሠልጣኞች በተሰጠው ሥልጠና እግዚአብሔርን በመፍራት ሕይወታችሁን እንድትመሩ፣ የተቀበላችሁትንም መክሊት በማትረፍ፣ በሄዳችሁበት ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ሀገራችሁን ማገልገል ይጠበቅባችኋል” በማለት የአደራ መልእክትና አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡

በሁለቱም ማስተባበሪያዎች በሁለት ዙር በተሰጡት ሥልጠናዎች ፷፩ ወንዶችና ፲፭ ሴቶች በድምሩ ፸፮ የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራር ሠልጣኞች ተሳትፈውበታል፡፡ በሥልጠና ቆይታቸውም ሠልጠኞቹ ስለ አገልግሎትና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚገጥሟትን ፈተናዎች ትሻገር ዘንድ የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲያበረክቱ ኀላፊነት እንዲሰማቸው ያደረገና ጥሩ ተሞክሮም ማግኘት እንዲችሉ የረዳቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡