ሆሣዕና በአርያም

ሆሣዕና የሚለው ቃል በዕብራይስጥ “ሆሼዕናህ” የሚል ሲሆን ትርጉሙም “እባክህ አሁን አድን” ማለት ነው፡፡ ይህ ቃል በዘመነ ብሉይ በቀደምት ነቢያት ዘንድ የተለመደ ቃል ነው፡፡ “አቤቱ እባክህ አሁን አድን፣ አቤቱ እባክህ አሁን አቅና፣ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩከ ነው፡ (፻፲፯፥፳፭-፳፮) እንዲል፡፡ የሆሣዕና በዓል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ የሚቀድሙትና የሚከተሉት ሕዝብ በተለይም አእሩግና ሕፃናት ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ፣ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፣ ሆሳዕና በአርያም በማለት ጌታችንን በክብር መቀበላቸው የሚታወስበት በዓል ነው፡፡ በዓሉም ሆሣዕና የሚለውን ስያሜ ያገኘው በዕለቱ ከተዘመረው መዝሙር ነው፡፡

ሆሣዕና በዐቢይ ጾም ስምንተኛ ሳምንት የሚከበር በዓል ሲሆን ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዓበይት በዓላት አንዱ ነው። ከስምንቱ የዐቢይ ጾም እሑዶች አንዱና የመጨረሻው ሳምንት ከትንሣኤ ቀድሞ የሚገኝ የሕማማት መግቢያ ዋዜማ ነው።

“አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ እጅግ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ እልል በዪ፤ እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም በአህያይቱም ግልገል በውርንጫይቱ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፡፡” (ዘካ. ፱÷፱) በማለት በነቢያት የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደብረ ዘይት ቤተ ፋጌ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱን በማሰብ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዓሉን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

ሰውን ከወደቀበት የበደል ጉድጓድ ያወጣው ዘንድ እግዚአብሔር ክንዱን ወደ ዓለም ላከ፡፡ ሰው ሆኖ የተገለጠው እግዚአብሔር ወልድ በጉድጓድ ተጥሎ የነበረውን በዚያም በሥጋ በነፍስ፤ በውስጥ በአፍአ ቆስሎ የነበረው አዳምን በትኅትና ሁለተኛ አዳም ሆኖ በሥጋ የቆሰለውን በለበሰው ሥጋ ቆስሎ፣ በነፍስ የታመመውን በትምህርቱ አዳነ፡፡ ከእርሱ አስቀድሞ ሰውን ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከባርነት ወደ ነፃነት የሚያመጣ ባለመኖሩ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ ለሰው መድኃኒት ሆነ፡፡ በሞቱም መድኃኒትነትን አደረገ፡፡ በነቢይ “እግዚአብሔር ለሕዝቡ መድኃኒትን ሰደደ፡፡” (መዝ. ፻፲፥፱) ተብሎ የተነገረው ተፈጸመ፡፡

ክርስቶስ ባለ መድኃኒት ሆኖ በኃጢአት ለታመሙ ደቂቀ አዳም ሁሉ ሕይወትን ይሰጥ ዘንድ ወደዚህኛው ዓለም መጣ፡፡ በምድራዊ ሥርዓት እንደምናየው መድኃኒትና ባለ መድኃኒት እንደሚለያዩ አይደለም፡፡ ሁለቱንም እርሱ በመምጣቱ (ሰው በመሆኑ) ፈጸመ እንጂ፡፡ መድኃኒት አድርጎ ሥጋውን ደሙን የሰጠ እርሱ ነው፡፡ በካህናት አድሮ ሰው በንስሓ ሲመለስ መድኃኒት ወደሆነው ወደ ራሱ የሚመራ እርሱ ነው፡፡

ክርስቶስ መድኃኒት መሆኑ በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ በእመቤታችን ማኅፀን የተጀመረው የእርሱ መድኃኒትነት እና ፍቅሩ ፍፃሜውን ያገኘው በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ መሐሪ ንጉሥ እርሱ መሆኑን ይገልጥ ዘንድ በፈቃዱ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡ ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም ከመግባቱ አስቀድሞ ከኢየሩሳሌም ፲፮ ምዕራፍ ያህል በምትርቀው በቤተ ፋጌ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ነበር፡፡

ከኢየሩሳሌም ለመግባት በደብረ ዘይት አጠገብ ወደ ቤተ ፋጌና ወደ ቢታንያ በደረሱ ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለቱን (ማለትም ጴጥሮስን እና ዮሐንስን) ላከ፡፡ እንዲህም አላቸው “በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፣ ወደ መንደርም በገባችሁ ጊዜ ሰው በላዩ ያልተቀመጠበት የዘህ ውርንጫ ታስሮ ታገኛላችሁ፤ ፍቱና አምጡልኝ፡፡” (ማር. ፲፩፥፪) በማለት አዘዛቸው፡፡ ሰው ወዳልገባባት የተዘጋች የምሥራቅ ደጅ ወደ ምትባል ወደ ድንግል መጥቶ ዘጠኝ ወር ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ እንደኖረ፤ ማኅየዊት ከምትሆን ሕማሙ በኋላም ሰው ባልተቀበረበት መቃብር እንደተቀበረ፤ አሁንም ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት ማንም ሰው ያልተቀመጠባቸውን በሌላ መንደር የሚገኙ አህያንና ውርንጫን እንዲያመጡ ደቀ መዛሙርቱን አዘዘ፡፡

የፍጥረት ሁሉ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በልደቱ እስትንፋሷን የገበረችለትን አህያ አሁን ደግሞ በፈቃዱ ስለ ሰው ሁሉ ሊሞት ሲል ንጉሥነቱን ሊያስመሰክርባት ወደደ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ካለው ፲፮ ምዕራፍ አሥራ አራቱን በአህያ ላይ ሳይቀመጥ በእግሩ ሄደ፡፡ ከዚያም ሁለቱን ምዕራፍ በአህያ ላይ በመቀመጥ ከተጓዘ በኋላ የኢየሩሳሌምን መቅደስ ሦስት ጊዜ በውርጫዋ ላይ በመሆን ዞረ፡፡ በዚህም ለሰው ሁሉ ያለው ቸርነቱ፣ ሕግ የተሰጣቸው አይሁድ እና ሕግ ያልተሰጣቸው አሕዛብ ላይ እኩል ቀንበርን መጫን እንዳይገባ አጠየቀ፡፡

ደቀ መዛሙርቱም የሰው ንብረት ዘርፈን እንዴት እናመጣለን?” ብለው መፍራታቸውን የተረዳው ጌታችንም “ምን ታደርጋላችሁ? የሚላችሁ ቢኖር ጌታቸው ይሻቸዋል በሉ፤ ያን ጊዜ ይሰዱአችኋል” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ሄደው ጌታችን ኢየሱስ እንዳዘዛቸው አደረጉ፡፡

ልብሳቸውንም በአህያውና በውርንጫይቱ ላይ አድርገው ጌታችንም በእነርሱ ላይ ተቀመጠ፡፡ ሕዝቡም ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉለት፤ ዘንባባ እና የዛፎችንም ጫፍ ጫፍ እየቆረጡ “ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ይጮሁ ነበር፡፡ (ማቴ. ፳፩÷፩-፲፩) ልብሳቸውን ማንጠፋቸውም ለክብሩ መግለጫ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ክብርና ምስጋና ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ከተማዋ በዝማሬና በአመስጋኞች ጩኸት ተናወጠች፡፡

የሕዝቡ ጩኸትና ደስታ ያበሳጫቸው ፈሪሳዊያንና አይሁድ የሚያመሰግኑትን ዝም እንዲያሰኝ ጌታችንን ቢጠይቁትም “እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ያመሰግኑኛል” ብሎ መልሶላቸዋል፡፡ በነቢዩ ዳዊት “ከሚጠቡ ሕፃናትና ከልጆች ምሥጋናን አዘጋጀህ” (መዝ. ፰÷፪) ተብሎ የተነገረው ትንቢት እንዲፈጸም የአርባ የሰማንያ ቀን የዓመት የሁለት ዓመት ሕፃናትም አመስግነውታል፡፡ አዋቂዎችም ሕፃናትም “ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ማመስገናቸው “መድኃኒት መባል ለአንተ ይገባሃል” ማለታቸው ነው።

በበዓለ ሆሣዕና ከሚነሣው ታሪክ ውስጥ የአህያዋና የውርንጫዋ ጉዳይ ነው፡፡ ጌታችን ኪሩቤል በሚሸከሙት ዙፋን የሚቀመጥ አምላክ ሲሆን ትሁት ሆኖ በአህያ ላይ ተቀመጠ፡፡ አህያዋን ከነውርንጫዋ “ፈታችሁ አምጡልኝ” ማለቱ የሰውን ልጅ ከኃጢአት እሥራት ለመፍታት የመጣ አምላክ መሆኑን ያመለክተናል፡፡ ደቀ መዛሙርቱም አህዮቹን ፈተው ማምጣታቸው ሥልጣነ ክህነታቸውን ያመለክታል፡፡ “በምድር የፈታችሁት በሰማይ የተፈታ ይሁን” እንዲል፡፡

በአህያ ላይ ልብሳቸውን ማንጠፋቸው የምትመች የማትቆረቁር የወንጌልን ሕግ ሰጠኸን ሲሉ ነው፡፡ በአህያ የተቀመጠ ሰው በፈረስ እንደተቀመጠ ሰው ፈጥኖ አያመልጥም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከፈለጉኝ አያጡኝም ሲል በአህያ ተቀምጧል፡፡

ከኢየሩሳሌም እስከ ቤተ መቅደስ ፲፮ ምዕራፍ ነው፡፡ ፲፬ቱን በእግሩ ሄዶ ሁለቱን በአህያዋ፣ በውርንጫይቱ ደግሞ ሦስት ጊዜ ቤተ መቅደሱን መዞሩ የሦስትነቱ ምሳሌ፣ አሥራ አራቱን በእግሩ መሄዱ አሥርቱ ትእዛዛትን፣ አራቱ ደግሞ የአራቱ ኪዳናት ማለትም ኪዳነ ኖኅ፣ ክህነተ መልከ ጼዴቅ፣ ግዝረተ አብርሃም እና ጥምቀተ ዮሐንስን ያመለክተናል፡፡

ከግለሰብ ደጅ የተፈታችን አህያ “ጌታዋ ይፈልጋታል” ብሎ ያስፈታት በፈጣሪነቱ ወይም ስለፈጠራት ገንዘቡ ስለሆነች ነው፡፡ አህያን ያልናቀ አምላክ እኛም ከኃጢአት ርቀን ብንፈልገው ማደሪያዎቹ ሊያደርገን ፈቃዱ ነው፡፡ የአህያዋን መፈታት የፈለገ ጌታ እኛም ወደ ካህናት ቀርበን ኃጢአታችንን ተናዘን ከበደል እሥራት እንድንፈታ ይፈልጋልና፡፡

ሆሣዕና ከረቡዕ ጀምሮ የሚታሰብ ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የበዓል ቀን እንደሆነ ይታወቃል። በዋዜማዎቹ ዕለታት ከቅዱስ ያሬድ ድርሰት ከሆነው ከጾመ ድጓ “ሆሣዕና በአርያም፣ ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት …’’ በማለት ይዘመራል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ ሕዝቡ ዘንባባ ይዘው “ቡርክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረክ ነው።’’ (መዝ. ፻፲፯፥፣፳፮) በማለት ስለተቀበሉት ይህን በማሰብ ቤተ ክርስቲያናችን ዘንባባ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ታድላለች፤ በቤተ ክርስቲያን በአራቱም ማዕዘናት ከአራቱም ወንጌል ዕለቱን የሚመለከቱ ምንባባት ይነበባሉ፡፡ ከቅዱስ ማቴዎስ (ማቴ. ፳፩፥፩-፲፯)፤ ከቅዱስ ማርቆስ (ማር. ፲፩፥፩-፲)፤ ከቅዱስ ሉቃስ (ሉቃ.፲፱፥፳፱-፴፰)፤ ከቅዱስ ዮሐንስ (ዮሐ. ፲፪፥፲፪-፳)።

በሰሙነ ሕማማት ጸሎተ ፍትሐት ስለማይፈጸም ጸሎተ ፍትሐት የሚደረገው በዚሁ ዕለት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ኒቆዲሞስ

ኒቆዲሞስ የሚለው ቃል የግሪክ ቃል ሲሆን፤ ድል ማድረግ ወይም አሸናፊነት ማለት ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ከፈሪሳዊውያን ወገን ነው፡፡ ፈሪሳውያን ሕግን የሚያጠብቁ፣ ሕዝብን የሚያስመርሩ፣ እነርሱ የማይፈጽሙትን ሕግ በሕዝብ ላይ የሚጭኑ፣ ራሳቸውን ከፍ ከፍ የሚያደርጉ፣ አባታችን አብርሃም እያሉ የሚመጻደቁ ነገር ግን የአባታቸው የአብርሃምን ሥራ ከማይሠሩት ወገን እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ፈሪሳውን ከመመጻደቃቸውም የተነሣ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከወግና ከልማድ ወጥተው ከጨለማ ወደ ብርሃን ይመለሱ ዘንድ የነፍስ ምግብ የሆነውን ወንጌልን ሲያስተምር፣ በተአምራቱ ድውያን ሲፈውስ፣ የተራቡትን አበርክቶ ሲያበላ፣ ውኃውን ወደ ወይንነት ሲለውጥና የተጠሙትን ሲያጠጣ በተመለከቱት ጊዜ ሕጋችንን ሻረ በማለት ሊገድሉት ይፈልጉ ነበር፡፡

ይህንንም ሲገልጥባቸው “ልትገድሉኝ ትሻላችሁ፤ እኔ በአባቴ ዘንድ ያየሁትን እናገራለሁ፤ እናንተም በአባታችሁ ያያችሁትን ታደርጋላችሁ” በማለት ከአባታቻው ከሰይጣን እንደሆኑ አላቸው፡፡ እነርሱም መልሰው “የእኛስ አባታችን አብርሃም ነው” አሉት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ አላቸው፡- “የአብርሃም ልጆች ብትሆኑስ የአብርሃምን ሥራ በሠራችሁ ነበር፡፡” (ዮሐ. ፰፥፴፱) በማለት ከሰይጣን እንደሆኑ ነግሯቸዋል፡፡  

ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ ብቻ ሳይሆን የአይሁድም አለቃቸው ነው፡፡ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትምህርትና ተአምራት ሰምቶና ተመልክቶ ቀን ቀን በአይሁድ ወንበር በሸንጎ እየዋለ በመምህርነቱ ሳይታበይ፣ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ፣ እውነትን ማግኘት ፈለጎ እንደ ባልንጀሮቹ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሳይቃወም በሌሊት ወደ እርሱ ዘንድ እየሔደ ወንጌልን ይማር ነበር፡፡ (ዮሐ. ፫፥፩) ሌሊትን ለምን መረጠ ቢሉ፡- መምህር ስለነበር ስማር ብዙ ሰዎች ሲያዩኝ በውዳሴ ከንቱ መምህር መባል ይቀርብኛል ብሎ፤ እንዳያዩትም ፈርቶ፣ ከቀን ይልቅ የሌሊት ልብ የተካተተ ስለሆነ በሙሉ ልቡ በማስተዋል ለመማር ስለፈለገ ከቀኑ ክፍለ ጊዜ ይልቅ የማታውን ክፍለ ጊዜ መረጠ፡፡ ሌሊት ጨለማ ነው፤ ብርሃን የለም ጨለማ የኃጢአት ምሳሌ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ በሌሊት መምጣቱ ኃጢአተኛ መሆኑንና በጌታችን ትምህርት አምኖ ንስሓ እንደሚፈልግ የሚያስረዳን ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ኒቆዲሞስ ከአይሁድ ተደብቆ በጨለማ ትምህርቱን ለመማር ከልቡናው ተነሣስቶ ወደ እርሱ ሲገሰግስ መምጣቱን ተመልክቶ ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” በማለት አስተማረው፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ምሥጢሩ አልተገለጠለትም ነበርና ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኀፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን? በማለት ለጌታችን ጥያቄ አቅርቧል፡፡ (ዮሐ. ፫፥፮፤ ፩ኛጴጥ. ፩፥፳፫)

እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስ የተወለደ መንፈስ ነውና፤  (ኤፌ. ፭፥፳፮) ብሎ ጌታችን ኢየሱስ ለኒቆዲሞስ ቢያስረዳውም ምሥጢሩ ሊገለጥለት ግን አልቻለም ነበር፡፡ ይህ እንደምን ይቻላል? በማለትም ጌታችንን ጠይቋል፡፡

ኒቆዲሞስ ቀድሞ በአደባባይ ሔዶ መማርን ቢፈራም በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምሥጢሩ ሲገለጥለት ምስክርነቱን መስጠት ጀመረ፡- መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና፡፡በማለት መሠከረ፡፡(ዮሐ. ፱፥፳፬፤ ሐዋ. ፲፥፴፰)

በመጨረሻም ኒቆዲሞስ አይሁድ ጌታችንን በቀራንዮ አደባባይ ያለ ኃጢአቱና በደሉ በምቀኝት በመስቀል ላይ በሰቀሉት ዕለት ፍርኃት ርቆለት ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበርም በቅቷል፡ “ፍጹም ፍቅር ፍርኃትን አውጥቶ ይጥላልእንዲል፡፡ (ማቴ. ፳፯፥፶፰፤ ፩ኛ ዮሐ. ፬፥፲፰)፡፡

የፈሪሳውያን አለቃና ምሁረ ኦሪት ከነበረው ኒቆዲሞስም ራስን ዝቅ ማድረግን፣ ጎደለንን ማወቅ፣ ለመልካም ነገር ልቡናን ከፍ ማድረግን፣ ሳፈሩና ሳሰቀቁ የእውነት ምስክር መሆንን፣ በሌሊት በጸሎትና በትምህርት መትጋትን፣ እስከ መጨረሻ በመጽናት አብነት መሆንን እንማራለን፡፡ በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህን  ታላቅ ሰው ለመዘከር የዐቢይን ጾም ሰባተኛው እሑድ በስሙ ሰይማ ታከብረዋለች፤ ተከታዮቿ ምእመናንም የእርሱን አሠረ ፍኖት እንዲከተሉ ትመክራለች፤ ታስተምራለችም፡፡

በዚህ በሰባተኛው ኒቆዲሞስ በተባለችው ሳምንት እሑድ የሚነበቡት ምንባባት (የቅዳሴ ምንባባት) የሚከተሉት ናቸው፡-

መልእክታት፡-

  • ሮሜ. ፯ ÷፩-፲፱
  • ፩ኛ ዮሐ. ፬ ÷ ፲፰-፳፩

ግብረ ሐዋርያት

  • የሐዋ.ሥራ ፭ ÷ ፴፬-፵፪

ምስባክ

  • መዝ. ፲፮ ÷ ፫-፬

ወንጌል፡-

  • ዮሐ. ፫÷፩-ፍጻሜው

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጀምሬአለሁ

በአዶና እንዳለ

የግድግዳው ሰዓት እየቆጠረ ነው። ግን ደግሞ ጊዜው እየሄደ አይደለም። ሌሊቶች እንዲህ ረዝመውብኝ አያውቁም። ከቤታችን ሳሎን መስኮት ጭላንጭል ብርሃንን እየጠበቅሁ ዓይኖቼን ከመጋረጃው ላይ መንቀል አቃተኝ። ለካ በእያንዳንዷ ማለዳ የምናያት ብርሃን ምን ያህል ትርጉም እንዳላት የምናውቀው ብርሃንን ስንናፍቅ ነው።

“ቤቴል፣ ቤቴል! ተነሽ እንጂ ነጋ እኮ!” ከነበርኩበት የሰመመን እንቅልፍ ያስወጣኝ የእናቴ ድምጽ ነበር።

እናቴ መጋረጃውን ስትከፍተው ያቺ ከመጋረጃው ሾልካ የገባችው የፀሐይ ብርሃን ግን እንደናፈቅኋት ሰላሜን ልትሰጠኝ አልቻለችም፤ ይልቁንም አስጨነቀችኝ። ከአልጋዬ ላይ ተስፈንጥሬ ተነሥቼ ስልኬን መጎርጎር ጀመርኩ፤ በይነ መረቡ ተጨናንቋል፣ ልቤ በፍጥነት ሲመታ ይታወቀኛል። እናቴ ሁኔታዬ ግራ አጋብቷት “ለምን አትረጋጊም? መሆን ያለበት ነገር ከመሆን ወደ ኋላ አይልም።” አለች በፍቅር ዓይኖቿ እየተመለከተቸኝ፡፡

እኔ ግን እናቴን ተረጋግቼ የማዳምጥበት ሁኔታ ላይ አልነበርኩም። ስልኬ ላይ እንዳፈጠጥኩ ሰዓታት ነጎዱ። “አይሠራም፤ አሁንም እየሠራ አይደለም” አልኩ ሳላስበው ቃላቶች አምልጠውኝ” ልቤ በአፌ ልትወጣ ደርሳለች።

“የኔ ልጅ አትጨነቂ! እግዚአብሔር ለአንቺ ያለውን አያስቀርብሽም ተረጋጊ” ብላ ጎንበስ ብላ ግንባሬን ስማ ፊቴን በቀኝ እጇ መዳፍ ዳበሰችኝ፡፡ እሷም የእኔ መጨነቅ እንደተጋባበት ታስታውቃለች፣ ነገር ግን እንት ናትና ልታረጋጋኝ ሞከረች፡፡

ከደቂቃዎች በኋላ ስልኬ ጮኸ። አባቴ ነበር። የምሞትበትን ቀን ሊያረዳኝ ይመስል እጄ በፍርሃት መንቀጥቀጥ ጀመረ። ራሴን እንደ ምንም አረጋግቼ ስልኩን አነሣሁት።

“ሄ…ሎ፣ ሄሎ ቤቴል!”  አጠራሩ የሐዘን ቅላጼ ነበረው።

“አ…ቤት”

“ውጤትሽን አይቼዋለሁ ለዩኒቨርሲቲ መግቢያ የሚሆን አላመጣሽም። ለሪሚዲያል ግን የሚሆን ነጥብ አምጥተሻል፡፡ ለመረጋጋት ሞክሪ እሺ?! … እባክሽ እየሰማሽኝ ነው አይደል? … ሄሎ ቤቴል ቤቴል …” አባቴን ለመስማት ዐቅም አልነበረኝም፡፡

ዓይኔን ስገልጥ ቀድሜ ያየሁት የእናቴን ፊት ነበር። ድንገት ከየት መጣ ያላልኩት ዕንባ ፊቴን ሲያርሰው ተሰማኝ። የእናቴን ፊት ማየት አልቻልኩም። ፊቴን አዙሬ ማልቀስ ጀመርኩ።

ታናሽ ወንድሜ ደንግጦ በፍርሃት ያስተውለኛል፡፡ ለማጥናት የማደርገው ጥረትና ድካሜን ያውቀዋል፡፡ የራሱን የወደፊት ውጤት ምን እንደሚሆን እያሰበ ስጋት የገባውም ይመስላል፡፡

“ቤቴል ልጄ ተይ እባክሽ እንደዚህ አትሁኚ፡፡ በቃ የእግዚአብሔር ፈቃድ አይደለም። ለምን ከእግዚአብሔር ጋር ትግል ትገጥሚያለሽ? ሁሉን ለበጎ የሚያደርግ አምላክ እኮ ነው።” ያዞርኩባትን ፊቴን መልሳ ወደ ራሷ አዙራ እቅፏ ውስጥ ሸጎጠችኝ። ማልቀስ ማቆም አቃተኝ።

እናቴ እቅፍ ውስጥ ሆኜ እንቅልፍ ወሰደኝ።

ለሳምንታት ከራሴ ጋር ስጣላ ቆየሁ። ነገን ሳስብ ድቅድቅ ጨለማ ይታየኝ ጀመር። በእኔ ሐዘንና ጭንቅት ሐሳብ ውስጥ የገቡት እናትና አባቴ መላ ፍለጋ መዳከር ጀመሩ። በርካታ ሐሳቦችን አውጥተው አውርደው ተነጋግረዋል፡፡ ነገር ግን ለሪሚዲያል መዘጋጅት እንዳለብኝና በርትቼ አጥንቼ በዩኒቨርሲቲው ለመቆየት እገዛ ሊያደርጉልኝ እኔን ለማግባበት ሞከሩ፡፡ እኔ ግን እጅግ ተጎድቻለሁ፣ ያልጠበቅሁት ውጤት ነበርና፡፡

ጊዜያት እየነጎዱ በሄዱ ቁጥር ከነበርኩበት ተስፋ ማጣትና ድብርት የሚያወጣኝን ትንሽዬ ተስፋዬን ለማስቀጠል ወሰንኩ። የተማርኳቸውን ኮርሶች ድጋሚ ተምሬ ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚያስገባኝን ነጥብ ማምጣት።

አማራጬ ይህ ነበር። ቀናት፣ ሳምንታት፣ ወራት አለፉ። ቀኑ ደርሶ ወደ ተመደብኩበት ጅማ ዩኒቨርሲቲ አቀናሁ። ከቤተሰቦቼ መለየት እንደ ሞት የምቆጥር ልጅ በዩኒቨርሲቲ ለብቻዬ ኑሮን መግፋት ግድ ሆነብኝ። ሳይደግስ አይጣላም አይደል የሚባለው በዚህ አጭር ቆይታዬ በፍጹም ልረሳቸው የማልችላቸውን ጓደኞች አፈራሁ። ሕይወት በአንድም በሌላም በኩል ታስተምራለችና።

የእኔ ራስን የመሆን የሕይወት ጉዞ የጀመረው እዚሁ ነው። በዩኒቨርሲቲ ለመቆየት የሚያሰችለኝን ውጤት ለማምጣት በተመደብኩበት ዩኒቨርሲቲ በነበረኝ የአራት ወራት የማካካሻ ትምህርቴን ቀጠልኩ፡፡

በሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ እንደማለፌ ራሴን ለማረጋገትና ግቢውን ለመልመድ የግቢ ጉባኤው ወንድሞችና እኅቶች ድጋፍ፣ ምክር የሚያስገርም ነበር፡፡ ዓርብ እስኪደርስ ይጨንቀኝ ነበር፡፡ የጸሎት ሥርዓቱ፣ ምክር አዘል ትምህርቱ፣ … ባይተዋር ከመሆን ታደገኝ፡፡ እግዚአብሔርም ረድቶኝ ጥሩ ውጤት ለማምጣት ቻልኩ። በውጤቴ እኔም ቤተሰቦቼም ደስተኞች ነበርን። “ሕይወት ብዙ አቅጣጫዎች አሏት!” ያለው ምን ነበር?

እኔም የሕይወት ጉዞዬን “ሀ” ብዬ ጀምሬአለሁ። በአሁኑ ወቅት የጅማ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዓመት የቅድመ ምሕንድስና ትምህርት ክፍል ተማሪ ነኝ። እርግጥ ነው ብዙ ያላየኋቸው ገና የማያቸው ብዙ ምዕራፎች እንደሚጠብቁኝ አውቃለሁ። ይህ ጅማሬ ነው። የሰው ልጅ የስኬቱ መነሻ አንድ እርምጃው ነው፤ እኔም ጉዞውን ጀምሬአለሁ፣ እደርሳለሁም፡፡ እያንዳንዳችን መድረስ እና መሆን የምንፈልገው ቦታ ላይ እስክደርስ ሁል ጊዜም ጀማሪዎች ነን። እኔም እነሆ ጀምሬአለሁ! ከእግዚአብሔር ጋር አሳካዋለሁም!!!

“ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አድርጉ።” (ማቴ. ፫፥፰)

በደሳለኝ ብርሃኑ

ክፍል አንድ

ንስሓ “ነስሐ” ከሚለው የግዕዝ ግሥ የወጣ ሲሆን ትርጉሙም ማዘን፣ መጸጸት፣ የኖርኩበት የኃጢአት ሕይወት ይበቃኛል ማለት፣ በደለኛነትን አምኖ ኃጢአትን ለካህን መናዘዝ ማለት ነው። ንስሓ እግዚአብሔርን መፈለግ ነው። ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ለይትፌሣሕ ልብ ዘየኀሦ ለእግዚአብሔር፤ እግዚአብሔርን የሚፈልግ ልብ ደስ ይበለው” (መዝ. ፻፭፥፫) በማለት እንደተናገረው።

ቅዱስ ዳዊት በዚህ ብቻ አያበቃም የአምላኩን ገጸ ምሕረት በመፈለግ “ስምዓኒ እግዚኦ ጸሎትየ ዘሰአልኩ ኀቤከ እምትሕዝብተ ጸላኢ አድኅና ለነፍስየ፤ አምላኪየ አምላኪየ እገይሥ ኀቤከ ጽምአት ነፍስየ ለከ። እፎ እስፋሕ ለከ ሥጋየ በምድረ በድው ኀበ አልቦ ዕፅ ወማይ ከመዝ በመቅደስከ አስተርአይኩከ፤ አቤቱ ጌታየ ሆይ ወደ አንተ የለመንኩትን ጸሎቴን ስማኝ፣ ነፍሴንም ከሚከታተሏት ከክፉ ጠላት አድናት፤ አምላኬ አምላኬ ወደ አንተ እገሠግሳለሁ፤ ነፍሴ አንተን ተጠማች፤ እንጨትና ውኃ በሌለበት ምድረ በዳ ሥጋዬን ለአንተ እንዴት ልዘርጋልህ? ኃይልህና ክብርህን ዐውቅ ዘንድ እንዲሁ በመቅደስ ውሰጥ ተመለከትሁህ” በማለት በፍጹም ንስሓ እና በተሰበረ ልብ አምላኩን ይማጸናል። (መዝ. ፷፫፥፩)።

ንስሓ ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝበት መንገድ ነው። እግዚአብሔር የጠፋውንና ከእርሱ የኮበለለውን አዳምን ፈልጎ ባገኘው ጊዜ በፍቅር በትከሻው እንደ ተሸከመው። ለዚህ ነው በተአምረ ማርያም መቅድም ላይ “ዘወፅአ እምኔኪ ኖላዊ ኄር ዘበአማን ዘኀሠሦ ለበግዕ ግዱፍ ወሶበ ረከቦ ጾሮ ዲበ መትከፍቱ፤ የጠፋ በግ አዳምን የፈለገው ባገኘውም ጊዜ የተሸከመው” የሚለው። አምላካችን ቸር ሰው ወዳጅ ስለሆነ የጠፋውን የሰው ልጅ ባገኘው ጊዜ አልተቆጣም ይልቁንም የእሱን በደል በትከሻው በመስቀል ላይ በመሸከም ፍቅሩን ገለጠለት እንጂ። ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያ በሥርዓተ ቅዳሴ ጸሎት ላይ “ነአኩቶ ለገባሬ ሠናያት ላዕሌነ እግዚአብሔር መሐሪ፤ ለእኛ በጎ ነገርን ያደረገ ይቅርባይ እግዚአብሔር አምላካችንን እናመሰግናለን” እንዳለው ንስሓ የእግዚአብሔር የቸርነቱ በር ናት። ቅዱስ ጎርጎርዮስ “የንስሓ በር ከፈተልን” እንዳለው (ሃይማኖተ አበው ፲፬፥፴)።

ንስሓ ነበር፡፡ ነገር ግን የሚገቡት ንስሓ ወደ ገነት ማስገባት አይችልም ነበር፡፡ ከአዳም ጀምሮ ሌሎቹም እግዚአብሔርን በማምለክ የነበሩ ሁሉ በእግዚአብሔር እጅ ይከለሉ /ይጠበቁ/ ስለነበር የሲዖል እሳት አይበላቸውም ነበር፡፡ ይህቺ የእግዚአብሔር የቸርነቱ በር ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከሚወለድ ድረስ ተዘግታ ነበር። ለዚህ ነው ጌታችንም “መዝጊያን አንኳኩ ይከፈትላችኋል” በማለት የቸርነቱን በር በንስሓ ያለማቋረጥ እና ያለ መሰልቸት እንድናንኳኳ ያዘዘን። (ማቴ. ፯፥፯)። ንስሓ በኃጢአት ትንሣኤ ፈውስ ናት። ኃጢአትን መሥራት እግዚአብሔርን ማጣት፣ ከእሱም መለየት፣ የዲያብሎስም ባሪያ መሆን ነው፣ በግብርም እሱን መምሰል ነው።

ኃጢአት መሥራት ከእግዚአብሔር መራቅ እንደሆነው ሁሉ፤ ንስሓ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር መመለስ ነው (ሚል. ፫፥፯)። ቅዱስ ዳዊት በተመለሰ ጊዜ “አቤቱ እንደ ቸርነትህ መጠን ማረኝ፤ እንደ ምሕረትህም ብዛት መተላለፌን ደምስስ፤ ከበደሌ ፈጽሞ እጠበኝ ከኃጢአቴም አንጻኝ፤ እኔ መተላለፌን አውቃለሁና ኃጢአቴም ሁል ጊዜ በፊቴ ነውና። አንተን ብቻ በደልኩ በፊትህም ክፋትን አደረግሁ” በማለት በቁርጥ ኅሊና የአምላኩን ምሕረት ተማጽኖአል (መዝ. ፶፥፩-፫)።

ንስሓ ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ነው። ከእግዚአብሔር በነቢዩ ኢዩኤል ላይ አድሮ “አሁንስ፥ ይላል እግዚአብሔር፥ በፍጹም ልባችሁ፥ በጾምም፥ በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ።
ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ አምላካችሁም እግዚአብሔር ቸርና መሓሪ፥ ቁጣው የዘገየ፥ ምሕረቱም የበዛ፥ ለክፋትም የተጸጸተ ነውና ወደ እርሱ ተመለሱ።” (ኢዩ. ፪፥፲፪-፲፫) በማለት ከኃጢአታቸው ቢመለሱ እግዚአብሔር ቸር፣ ይቅር ባይ፣ መሓሪም መሆኑን ይገልጻል፡፡  

ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ንስሓ እንደ እሳት ሆና ስለምታቃጥለው ንስሓን ይጠላል። ምክንያቱም ንስሓ ዲያብሎስ በሰው ልጆች ሕይወት ውስጥ የገነባውን ግንብ የምታፈርስ መዶሻ ናትና። ለዚህም ነው ዲያብሎስ ሰው ኃጢአት ሲሠራ በእግዚአብሔር ቸርነት እንዲያመካኝ ያደርግና በኃጢአቱ ተጸጽቶ ንስሓ ሊገባ ሲል ደግሞ “ይህን ሁሉ በድለህ እግዚአብሔር አይምርህም” በማለት የንስሓ ዕድል እንዳያገኝ የንስሓን በር ይዘጋበታል። በዚህም ተስፋ በማስቆረጥ የራሱን ምርኮ ያበዛል። ስለዚህ “በሰይጣን እንዳንታለል፤ የእርሱን ሐሳብ አንስተውምና” እንዳለው ቅዱስ ጳውሎስ ተንኮሉን ዐውቀን ልንነቃበት ይገባል (፪ኛቆሮ. ፪፥፲፩)።

ኃጢአትን የምንናዘዘው ደግሞ ለካህን ነው። ካህን ስንልም ቤተ ክርስቲያን የምታውቀው፣ በአገልግሎት ያሰማራችውና አድራሻው የሚታወቅ መሆን አለበት። አገልግሎቱን በአግባቡ ለማግኘትና በቅርበት ለመከታተልም የንስሓ አባት መያዝ የሚገባው ከሚገለገሉበት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ነው።

ንስሓ ከምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አንዱ ስለሆነ የሚፈጸመውም በቤተ ክርስቲያን ነው። አንድ ተነሳሒ ለካህኑ የሚናዘዘው ካህኑን እንደ እግዚአብሔር መልእክተኛ አድርጎ እግዚአብሔርን ደግሞ ዳኛ አድርጎ ነው። “ካህኑ የሠራዊት ጌታ የእግዚአብሔር መልእክተኛ ነውና” እንዲል (ሚል. ፪፥፯)። ኑዛዜውንም በዝርዝር ሳይደብቅና ሳያድበሰብስ መናዘዝ አለበት። ለምሳሌ ሕዝበ እሥራኤል በኢያሱ ዘመን ዮርዳኖስን ተሻግረው መጀመሪያ ከወረሷት ከኢያሪኮ ምድር ምንም ነገር እንዳይወስዱ እርም ነውና አትንኩ ተብለው ታዘው ነበር። ነገር ግን አካን የተባለው ሰው ከተከለከለው ሰርቆ በመውሰዱ ተጣርቶ እሱ መሆኑ ተደረሰበት። በዚያን ጊዜ ኢያሱ አካንን እንዲህ አለው:- “ልጄ ሆይ፥ ለእስራኤል አምላክ ለእግዚአብሔር ክብር ስጥ፥ ለእርሱም ተናዘዝ፤ ያደረግኸውንም ንገረኝ፤ አትሸሽገኝ” አለው።  አካንም መልሶ ኢያሱን፡- “በእውነት የእስራኤልን አምላክ እግዚአብሔርን በድያለሁ፤ እንዲህና እንዲህም አድርጌአለሁ። በዘረፋ መካከል አንድ ያማረ የሰናዖር ካባ፥ ሁለት መቶም ሰቅል ብር፥ ሚዛኑም አምሳ ሰቅል የሆነ ወርቅ አይቼ ተመኘኋቸው፥ ወሰድኋቸውም፤ እነሆም፥ በድንኳኔ ውስጥ በመሬት ተሸሽገዋል፥ ብሩም ከሁሉ በታች ነው አለው።”(ኢያ. ፯፥፲፱-፳፩) በማለት ያደረገውን በዝርዝር ለኢያሱ ተናዘዘ። ይህም የሠሩትን ኃጢአት በዝርዝር ለንስሓ አባት መናገር ተገቢ መሆኑን እንረዳለን።

 በሐዲስ ኪዳንም ስንመለከት ዮሐንስ ሕዝቡን ሲያጠምቅ “ያን ጊዜ ኢየሩሳሌም ይሁዳም ሁሉ በዮርዳኖስም ዙሪያ ያለ ሀገር ሁሉ ወደ እርሱ ይወጡ ነበር። ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር።” በማለት የኑዛዜን ተገቢነት ያስረዳናል (ማቴ. ፫፥፭-፮)። በዘመነ ሐዋርያትም ኑዛዜ እንደ ነበረ ሲገልጽ “አምነውም ከነበሩት እጅግ ብዙ ሰዎች ያደረጉትን እየተናዘዙና እየተናገሩ ይመጡ ነበር” በማለት ይመሰክራል (ሐዋ. ፲፱፥፲፰)። ጌታችንም አንድ ለምጽ የነበረበትን ሰው ቀርቦ “ጌታ ሆይ ብትወድስ ልታነጻኝ ትችላለህ” እያለ እየሰገደ በጠየቀው ጊዜ እጁን ዘርግቶ ዳሰሰውና “እወዳለሁ ንጻ” አለው። ወዲያውም ከለምጹ ዳነ። ጌታችንም “ለማንም እንዳትናገር ተጠንቀቅ! ነገር ግን ሄደህ ራስህን ለካህን አሳይ” አለው። (ማቴ. ፰፥፪-፬)።

ዳግመኛም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተአምረ ኢየሱስ ላይ ስሟ ብርስፌንያ የተባለችውን ሳምራዊቷን ሴት ለብቻዋ አነጋግሯት ኃጢአቷን እንድትናዘዝ አደረጋት (ዮሐ. (፬፥፩-፵፪)። በዚህም ንስሓ አባት ቀስ አድርጎ ለብቻ በጥበብና በጥንቃቄ ተነሳሒን ማናገርና ማስተናገድ እንደሚገባ ለማጠየቅ ነው።

የንስሓ መንገዶችና አፈጻጸሙ

አንድ ሰው ንስሓ ከመግባቱ በፊት በደላኛነቱን ወይም ኃጢአተኛነቱን ማመን አለበት። የራሱን ኃጢአትና የእግዚአብሔርን ቸርነት ማሰብ አለበት። ምንም እንኳ ኃጢአተኛ ቢሆን እግዚአብሔር ይምረኛል ይቅር ይለኛል ማለት ይገባዋል እንጂ ተስፋ መቁረጥ የለበትም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ተስፋ የሚቆረጥበት ሳይሆን የተቆረጠው ተስፋ የሚቀጠልበት አምላክ ነው እንጂ። ለዚህ ነው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ወይእዜኒ መኑ ተስፋየ አኮኑ እግዚአብሔ፤ አሁንስ ተስፋዬ ማነው እግዚአብሔር አይደለምን? (መዝ. ፴፰፥፯) ያለው። ስለዚህ ኃጢአት መጀመሪያ የሚናዘዘው ለራስ ነው፤ የንስሓ የመጀመሪያ ደረጃም ትንሣኤ ልቡና ወይም ንስሓ ለመግባት መፈለግ ነው። “በፊተኛው ትንሣኤ ዕድል ያለው ብፁዕና ቅዱስ ነው፤ ሁለተኛው ሞት በእነርሱ ላይ ሥልጣን የለውም” (ራእ. ፳፥፮) እንዲል። የመጀመሪያው ትንሣኤ (ትንሣኤ ልቡና) ከኋለኛው ሞት ያድናል። ።

 በሉቃስ ወንጌል ፲፭ ላይ የጠፋው ልጅ ታሪክ የሚያስተምረን ይህንኑ ነው። “ወደ ልቡም ተመልሶ እንዲህ አለ” የሚለው ዐረፍተ ነገር በኃጢአት ውስጥ መሆኑን ተረዳ፣ ልብ አደረገ የሚለው ሲሆን፣ “ተነሥቼ ወደ አባቴ ልሂድ። አባቴ ሆይ በሰማይና በፊትህ በደልኩ፤ ወደ ፊትም ልጅህ ልባል አይገባኝም፤ ከአገልጋዮችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እለዋለሁ” ብሎ ለራሱ መናገሩ ደግሞ ለማድረግ መወሰኑን ያመለክታል። ወስኖም አልቀረ “ተነስቶም ወደ አባቱ መጣ” እንዳለው የወሰነውን በተግባር አደረገ። ስለዚህ የንስሓ መንገድ ኃጢአት ውስጥ መሆናችንን መንቃት፣ ንስሓ ለመግባት መወሰንና ንስሓ አባት መያዝ፣ ቀጥሎም ንስሓ መግባት ነው፡፡

ሦስተኛ ኃጢአትን መናዘዝ ነው። በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት መሠረት ተነሳሒው ከካህኑ ጋር ፊት ለፊት እየተያዩ መናዘዝ አለበት። ስለ ኃጢአቱም እንዲሰቀቅና በዚህም የሚገኘውን መንፈሳዊ ጸጋ እንዲያገኝ ያደርጋል። ስንናዘዝም ኃጢአትን እንደ ጀብድ በመቁጠር ወይም በትዕቢት ሳይሆን ራስን በእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ “ቀና ብዬ የሰማዩን ርዝመት አይ ዘንድ አገባቤ አይደለም” (ጸሎተ ምናሴ) በማለት መሆን አለበት። ካህናት “አዕይንተ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ዓይኖች” ናቸው። በካህኑም አድሮ የኃጢአትን ይቅርታ የሚሰጠን እግዚአብሔር ነው። ለዚህ ነው ካህናትም ኑዛዜ ከሰጡ በኋላ “እግዚአብሔር ይፍታ” የሚሉት።

የሰይጣን ተንኮል የሰው ልጅ ያለ መሰቀቅ እና ያለ ፍርሃት ኃጢአትን እንዲሠራ ያደርግና ኃጢአትን አምኖ ንስሓ እንዲገባ ደግሞ ዕድል አይሰጠውም፤ እግዚአብሔርን ጨካኝ ያስመስለዋል። ስለዚህ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ እንዳለው “ካህኑን እንደ መንፈሳዊ አባትነቱ እየው። ልክ በሽተኛ የተሸፈኑ ቁስሎችን ገልጦ ለሐኪም እንደሚያሳይና እንደሚፈወስ ምሥጢሮችህን በግልጽ ንገረው” ኑዛዜን በካህኑ ፊት በአግባቡ መፈጸም ይገባል። እግዚአብሔር ሁሉን አዋቂ ነውና ሰው ኃጢአቱን ከእግዚአብሔር ፊት መደበቅ አይችልም። በእግዚአብሔር ፊት ሁሉ ነገር እንደ አሁን የተገለጠ ነው፤ ከእርሱ የተሰወረ ነገር የለምና።

ስለዚህ ኃጢአትን ለመናዘዝ ማፈር ሁል ጊዜ ሰይጣን እየከሰሰው ኃጢአቱም እየወቀሰችው ለመኖር መፍቀድ ነው። ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ አርጋኖን ዘረቡዕ ላይ “ኃጢአቴን ለመናገር ለምን አፍራለሁ? አለመናዘዜስ ለምንድነው? የሚከሱኝ ጠላቶቼ የሚመሰክሩብኝ ኃጢአቶቼ ሳሉ እንግዲህ ኃጢአቴን እናገራለሁ የተሰወረውን በሚያይ አፍ የተናገረውን ልቡና የመከረውን መርምሮ በሚያውቅ በልዑል እግዚአብሔር በዓይኖቹ ፊት የተገለጸ ሲሆን እኔ ለምን እሰውረዋለሁ” ይላል። “እኛ ኃጢአታችንን ስንደብቅ እግዚአብሔር ይገልጥብናል፤ እኛ ስንናዘዝ ደግሞ እግዚአብሔር ይሸፍንልናል” እንዳለው አባ መቃርዮስ ኃጢአትን ለመሰወር መሞከር ሌላ ኃጢአትን ይጨምራል።

ከዚህ ላይ የቅዱስ ዳዊትን ታሪክ መመልከት ጉዳዩን በደንብ ግልጽ ያደርግልናል። ዳዊት ሥራ ፈትቶ በሰገነቱ ላይ ሲመላለስ የኦርዮ ሚስት ገላዋን ስትታጠብ ተመለከታት፤ በልቡም ተመኛት፤ አስነወራትም። የራሱ ካልሆነች ሴት ጋር ተኛ ዝሙትን ፈጸመ። ይህንን ኃጢአቱን ለመሰወር ሲል ኦርዮን ከጦር ሜዳ አስጠርቶ በልቶ ጠጥቶ ታጥቦ ከሚስቱ ጋር እንዲተኛ ቢያባብለውም ኦርዮ ግን እምቢ አለ። “የእግዚአብሔር ታቦት በጠላት ተማርካ ሕዝበ እግዚአብሔር በጦርነቱ እየተማገዱ እኔ ገብቼ ከሚስቴ ጋር እንዴት እተኛለሁ?” አለው። ኦርዮ ንጉሡ ዳዊትን አሳፈረው። ዳዊትም መልእክተኞቹን ልኮ ኦርዮ በጦር ሜዳ እንዲሞት አደረገው። አንዱን ኃጢአቱን ለመደበቅ ሌላ የከፋ ኃጢአትን ጨመረ።

ነገር ግን የሰውን ጥፋት የማይወድ እግዚአብሔር ለነቢዩ ዳዊት ነቢዩ ናታንን ላከለት። ናታንም ንጉሥ ዳዊትን በፈሊጥ ተናገረው። “ንጉሥ ሆይ አንድ ሰው መቶ በጎች ነበሩት፣ አንዲት በግ የነበረችው ሰው ደግሞ ወደ ሩቅ መንገድ ለመሄድ አንዲቱን በጉን ለባለ መቶ በጎች ሰው አደራ አስጠበቀው። መቶ በጎች ያሉትም ሰው እንግዳ መጣበት፣ ያቺን የአደራ በግ አደራውን በልቶ ለእንግዳው አረደለት። ነቢዩ ናታንም ንጉሥ ዳዊትን አለው፣ ንጉሥ ሆይ ይህ ሰው ፍርድ ይገባዋል ወይስ አይገባውም?” አለው። ንጉሥ ዳዊትም “ይህ ሰው ምናምንቴ ነው አራት እጥፍ ፍርድ ይገባዋል” አለ። ነቢዩ ናታንም መልሶ “ንጉሥ ሆይ በራስህ ላይ ፈረድህ” አለው። ባለ መቶ በግ የተባለው ዳዊት ነው፤ ዳዊት ብዙ ሚስቶች ነበሩትና። ባለ አንድ በግ የተባለው ኦርዮ ነው። እንግዳ መጣበት የተባለው የሥጋ ፍላጎቱ ነው። አርዶ እንግዳውን አስተናገደበት የተባለው የኦርዮን ሚስት ማስነወሩ ነው። ዳዊት ይህ ሰው ምናምንቴ ነው አራት እጥፍ ይክፈል ያለውም ራሱ ከአራት በላይ ቅጣት ተቀጣ።

 በዝሙት ከኦርዮ ሚስት ከቤርሳቤህ የተወለደው ልጁ ሞተ፤ አምኖን የተባለው ልጁ የገዛ እኅቱን በመድፈር ከክብር አሳነሳት፣ በቁሟ ገደላት፤ ንጉሡንም በተከበረበትና በነገሠበት ሀገር አዋረደው፤ የተደፈረችው ልጅ የትዕማን ወንድም አቤሴሎም እንዴት በእኅቴ ላይ እንዲህ ያለውን ነውር ተግባር ታደርግባታለህ ብሎ አምኖንን ገደለው። በመጨረሻም የዳዊት የገዛ ልጁ ከመንበሩ አባረረው። ዳዊት ኃጢአቱን ለመሰወር ብሎ እጥፍ ቅጣት ተቀጣ። (፪ኛሳሙ. ፲፩ እና ፲፪).

“ኃጢአቱን የሚሰውር አይለማም። የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምሕረትን ያገኛል”(ምሳ. ፳፰፥፲፫) እንዳለው እግዚአብሔር እንዳያስብብን አስቀድመን በደላችንን ማሰብ ተገቢ ነው። “የተገለጠውን ትሸፍነዋለህ፣ የተሸፈነውን ትገልጠዋለህ” እንዳለው ቅዱስ ኤፍሬም ሰው ኃጢአቱን ሲያስብ እግዚአብሔር ይረሳለታል፤ ሰው ኃጢአቱን ሲዘነጋ ግን እግዚአብሔር ያስታውስበታል። ጻፎችና ፈሪሳውያን ስታመነዝር አገኘናት ብለው ወደ ጌታ ያመጧትን ሴት ጌታ አልፈርድብሽም ሂጂ አላት (ዮሐ. ፰)። እግዚአብሔር በሾመው ካህን ፊት ኃጢአትን ለመሸሸግ መሞከር ከእግዚአብሔር ዓይኖች ለመደበቅ መሞከር ነው። ምክንያቱም ካህናት የእግዚአብሔር ዓይኖች ናቸውና። ሰው ንስሓ ሲገባ በማሰብ፣ በመናገር፣ በተግባር የሠራውን ኃጢአት መናዘዝ አለበት። ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በተግሳጹ “በበደሉ ላይ ድፍረትንና ሽንገላን ቢጨምር ከዚያች ኃጢአት መጠበቅ አልችልም። እርስዋን በሚመስል ኃጢአት ከመውደቅም አይድንም” እንዳለው ኃጢአትን በአፍ ብቻ እየረገሙ በተግባር ደግሞ መፈጸም ራስን ማታለል ስለሆነ ኃጢአትን የጠላት ንስሓ ገብቶ ከእርሱ ያርቃታል። ስንሠራው ያላፈርነውን ኃጢአት ለካህን ስንናዘዝ ማፈር የለብንም። በነውር መሰቀቅ የሥራ ዋጋ ነውና።

“በኋላ በፍርድ ቀን በሰማይና በምድር ንጉሥ ፊት ከምናፍር በአንድ ካህን ፊት ማፈር ይሻላል” እንዳለው ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ። እግዚአብሔር በፍርድ ቀን በአደባባይ ይጠይቀናል። ስለዚያች ስለ ፍርድ ቀን ቅዱስ ባስልዮስ በውዳሴ አምላክ ዘሠሉስ ጸሎት ላይ “ፍጥረትም ሁሉ የኃጢአት ሸክም ተሸክሞ በሚያስፈራ ዙፋንህ ፊት በሚቆሙበት ጊዜ የሠሩትን ክፉውንም በጎውንም ሁሉ ያን ጊዜ ሥራችን ይታወቃል። ምሥጢራችንም ይወጣል። መጋረጃችንም ይገለጣል። አቤቱ የኃሣራችንና የኃፍረታችን ደብዳቤ በመላእክት ፊት ይዘረጋል። ሥራችን ሁሉ በፍጥረት ሁሉ መካከል ይነበባል። አቤቱ ጌታዬ ሆይ የዚያች ሰዓት ግርማዋ ምን ያህል ይሆን!” ይላል።

በኑዛዜ ወቅት ለኃጢአት ምክንያት መደርደር፣ ያለ ጸጸት መናዘዝና በሰው ማሳበብን ማስወገድ ይገባል። አዳም አባታችን ኃጢአቱን ብቻ ከመናገር ይልቅ ለኃጢአቱ ምክንያት መደርደርና ክስ ጨመረበት። ንስሓ ደግሞ የራስን ኃጢአት መናገር እንጂ የሰውን በደል መዘርዘር አይደለም።

ዐራተኛው ኃጢአትን መተውና ኃጢአትን ከሚቀሰቅሱ ነገሮች መራቅ ነው። እሳት ዳር ተቀምጦ እሳቱ አይንካኝ እንደማይባል ሁሉ ከኃጢአት መንገድም መራቅ ይገባል። “ንስሓ በጥምቀት ከእግዚአብሔር ከምትገኝ ልጅነት ሁለተኛ መዓርግ ናት። በሃይማኖት ገንዘብ ያደረግነው የመንግሥተ ሰማይ መያዣ ናት፤ ለሚሿት ሰዎች የተከፈተች የይቅርታ በር ናት። በንስሓ በርነት ከፈጣሪ ወደሚገኝ ቸርነት እንቀርባለን።

መከላከያ ከሚሆን ከንስሓ ርቀን ይቅርታን አናገኝም። ንስሓ እግዚአብሔርን በመፍራትና በሃይማኖት በልቡና የምትገኝ ሁለተኛ ጸጋ ናት። ቀዛፊዋ እግዚአብሔርን መፍራት በሚሆን በንስሓ መርከብ ካልተሳፈርን ኅሊና ጸንቶበት በእኛና በፍቅረ እግዚአብሔር መካከል ያለ ሽታው የከፋ ይህን ዓለም ሰንጥቀን ማለፍ አይቻለንም።” (ማር ይስሐቅ አንቀጽ ፳፮)

አምስተኛው፡- ቅዱስ ዳዊት እንዳለው “በእንተዝ ኵሎ ፍኖተ ዐመፃ ጸላእኩ፤ የሐሰትን መንገድ ጠላሁ” (መዝ. ፻፲፰፥፻፬) እንዳለው ኃጢአትን መጥላት ነው። ኃጣውእን የጠላ ሰው ኃጢአት መሥራት ያቆማል። በኃጢአቶቹም የተናዘዘ ሰው ሥርየትን ያገኛል። መጀመሪያ ከኃጢአት ጋር ጠላትነትን ማድረግ ያልቻለ ሰው ኃጢአት የመሥራት ልማዱን መተው አይችልም። ያለ ኑዛዜም ሥርየተ ኃጢአትን ሊያገኝ አይችልም። ምክንያቱም ኃጢአትን ሳያፍሩ መናዘዝ የእውነተኛ ትሕትና ምክንያት ነውና” ይላል አብርሃም ሶርያዊው፡፡

ስድስተኛው፡- የንስሓ ፍሬ ማፍራት ነው። “እንግዲህ ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አድርጉ” (ማቴ. ፫፥፰) እንዳለው በሰረቀበት እጁ መመጽወት፣ ዝሙትን ትቶ መጸለይ፣ በጎነትን መጨመር ይገባል። ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ “በጎ ለማድረግ ዐውቆ ለማይሠራው ኃጢአት ነው”(ያዕ. ፬፥፲፯) እንዳለው የመንፈስ ፍሬዎች የተባሉትን ማፍራት ይገባል። (ገላ. ፭፥፳፪)።

ሰባተኛው፡- መቁረብ ነው። ሁሉም ክርስቲያን መቁረብ አለበት። ስንቆርብ ደግሞ ተዘጋጅተን ነው እንጂ በቅተን አይደለም። ቅድስና እንኳ ቢኖረን የክርስቶስን ሥጋና ደም ለመቀበል ብቁ የሚሆን የለም። “ነገር ግን ንስሓ ገብቶ መዘጋጀት ይገባል።  ስለዚህ ሳይገባው ይህን እንጀራ የበላ ወይም የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ጽዋ የጠጣ ሁሉ የጌታ ሥጋና ደም ዕዳ አለበት።  ሰው ግን ራሱን ይፈትን፥ እንዲሁም ከእንጀራው ይብላ ከጽዋውም ይጠጣ፤ ሳይገባው የሚበላና የሚጠጣ የጌታን ሥጋ ስለማይለይ ለራሱ ፍርድ ይበላልና፥ ይጠጣልምና።” እንዳለው ቅዱስ ጳውሎስ፡፡ (፩ቆሮ. ፯፥፳፯-፳፱)

ይቆየን

“ታማኝአገልጋይማነው?” (ማቴ. ፳፬፥፵፭)

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት የዐቢይ ጾም ስድስተኛው ሳምንት ገብር ኄር ይባላል፡፡ ሰያሜውንም የሰጠው ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በሆነው ጾመ ድጓ በተባለው መጽሐፍ የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህም መሠረት በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብር ኄር ወይም ታማኝ አገልጋይ ላይ ትኩረት ያደርጋል፡፡

ይህንንም ወንጌላው ቅዱስ ማቴዎስ እንዲህ እያለ ይገልጸዋል፡፡ “መንገድ እንደሚሄድ አገልጋዮቹንም ጠርቶ ሊያተርፉበት ገንዘቡን እንደሰጣቸው ሰው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ችሎታው ለአንዱ አምስት፣ ለአንድ አምስት፣ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ያ አምስት መክሊት የተቀበለውም ሄደ፤ ነግዶም ሌላ አምስት መክሊት አተረፈ፡፡ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ወርቅ ቀበረ፡፡” (ማቴ. ፳፭፥፲፬-፲፰)

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ይቆጣጠራቸው ዘንድ ተመልሶ መጣ፡፡ “ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር ላይ እምነት ያገኝ ይሆን?” እንዲል በእነዚህ አገልጋዮች አንጻር ምእመናን ለእግዚአብሔር ያላቸውን እምነትና ታማኝነት፣ ታምኖም መኖር ምን ያህል እንደሆነ የሚያመለክት ነው፡፡ (ሉቃ. ፲፰፥፰)

አገልጋዮቹም ከጌታቸው የተቀበሉትን መክሊትና ያተረፉትን ይዘው በተራ ቀረቡ፡፡ በቅድሚያም አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና፡- “አቤቱ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት አተረፍሁ፤ ብሎ አምስት መክሊት አስረከበ፡፡ ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም መጥቶ፡- አቤቱ ሁለት መክሊትን ሰጥተኸኝ አልነበረምን? እነሆ ሌላ ሁለት መክሊትን አተረፍሁ አለ፡፡ ጌታውም፡- መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡” ሁለቱም የተሰጣቸውን መክሊት ተጠቅመው ወጥተው ወርደው ሠርተውና አትርፈው ተገኝተዋልና ያገኙትንም ይዘው በመቅረብ ከጌታቸው ዘንድ ሞገስና ክብርን አግኝተዋል፡፡

ጌታው ሠርቶ፣ አገልግሎ ያተርፍበት ዘንድ አንድ መክሊት የተሰጠው አገልጋ ግን ከሁለቱ በተለየ መንገድ ወደ ጌታው ቀረበ፡፡ “አንድ መክሊት የተቀበለውም መጣና እንዲህ አለ፡- አቤቱ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሄድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤ እንግዲህ እነሆ መክሊትህ” አለው፡፡  ጌታውም መልሶ አለው፡- “አንተ ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እኔ ካልዘራሁበት የማጭድ ካልበተንሁበት የምሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንሁ ታውቃለህ? ገንዘቤን ለለዋጮች መስጠት በተገባህ ነበር፤ እኔም ራሴ መጥቼ ገንዘቤን ከትርፉ ጋር በወሰድሁ ነበር፡፡ የቆሙትንም እንዲህ አላቸው፡- ይህን መክሊት ከእርሱ ተቀብላችሁ ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ሁሉ ይሰጡታልና ይጨምሩለታልም፡ ለሌለው ግን ያንኑ ያለውን ይወስዱበታል፡፡ ክፉውን አገልጋይ ግን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት በውጭ ወደአለ ጨለማ አውጡት፡፡” (ማቴ. ፳፭፥፲፬-፴) አለ፡፡

ባዕለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፡፡ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው፤ መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት በዕለተ ምጽአት ለሁሉም በአገለገለው አገልግሎት ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ የሚያሳይ ነው፡፡

ያገለገሉትና ታምነው የተገኙት ወደ ጌታህ ደስታ ግባ ማለቱ ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርሱ፤ ሰነፎች ደግሞ ጥርስ ማፋጨት፣ ስቃይ፣ ጽኑዕ ጨለማ ባለበት ሲዖል መውረዳቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

ነቢያት፣ ጻድቃን ሠማዕታት፣ ቅዱሳን በታማኝ አገልግሎታቸው ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ሊቀ ነቢያት ሙሴ፣ ዮሴፍ፣ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት፣ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ጳውሎስን ማንሣት የምንችል ሲሆን፤ ለጌታቸው ያልታመኑት ደግሞ ይሁዳ፣ ሐናንያ፣ ሰጲራ፣ የመሳሰሉት የደረሰባቸውን ጉዳት መጥቀስ ይቻላል፡፡

ለዚህ ነበር ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ አድነኝ ደግ ሰው አልቋልና፤ ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሏልና” በማለት የገለጸው፡፡ (መዝ. ፲፩፥፩) ስለዚህ ሁሉም በየአለበት የአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ “አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሀለሁ” የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል መስማት ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን መንግሥቱን እንድንወርስ፣ “ገብርኄር” እንድንባል አምላካችን ይርዳን፡፡

የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)

“መኑ ውእቱ ገብር ኄር ወምእመን ዘይረክቦ እግዚኡ በምግባረ ሠናይ ወይሰይሞ ዲበ ኲሉ ንዋዩ፡፡ ካዕበ ይቤሎ እግዚአብሔር ገብር ኄር ወምእመን ዘበውኁድ ወምእመን ዘበውኁድ ምእመነ ኮንከ ዲበ ብዙኅ እሰይመከ ባዕ ውስተ ፍሥሐሁ ለእግዚእከ፡፡

ትርጉም፡– “ጌታው መልካም ሲሠራ አግኝቶ በገንዘቡ ሁሉ ላይ የሚሾመው ቸርና ታማኝ አገልጋይ ማን ነው? ዳግመኛም እግዚአብሔር በታናሹ የታመንህ ደግና ታማኝ አገልጋይ ሆይ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው፡፡

 መልእክታት

የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት፡– (፪ኛጢሞ. ፪፥፩፲፮)

“እንግዲህ፥ ልጄ ሆይ፥ አንተ በክርስቶስ ኢየሱስ ባለው ጸጋ በርታ። ብዙ ሰዎች የመሰከሩለትን ከእኔም የሰማኸውን ሌሎችን ደግሞ ሊያስተምሩ ለሚችሉ ለታመኑ ሰዎች አደራ ስጥ። እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ወታደር ሆነህ፥ አብረኸኝ መከራ ተቀበል። የሚዘምተው ሁሉ ለጦር ያስከተተውን ደስ ያሰኝ ዘንድ ትዳር በሚገኝበት ንግድ ራሱን አያጠላልፍም። ደግሞም በጨዋታ የሚታገል ማንም ቢሆን፥ እንደሚገባ አድርጎ ባይታገል፥ የድሉን አክሊል አያገኝም። የሚደክመው ገበሬ ፍሬውን ከሚበሉት መጀመሪያ እንዲሆን ይገባዋል። …”

የሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ መልእክት፡– (፩ኛጴጥ. ፭፥፩፲፪)

“እንግዲህ እኔ፥ ከእነርሱ ጋር ሽማግሌ የክርስቶስም መከራ ምስክር ደግሞም ሊገለጥ ካለው ክብር ተካፋይ የሆንሁ፥ በመካከላቸው ያሉትን ሽማግሌዎች እመክራቸዋለሁ፤ በእናንተ ዘንድ ያለውን የእግዚአብሔርን መንጋ ጠብቁ፤ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በውድ እንጂ በግድ ሳይሆን፥ በበጎ ፈቃድ እንጂ መጥፎውን ረብ በመመኘት ሳይሆን ጐብኙት፤ ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ እንጂ ማኅበሮቻችሁን በኃይል አትግዙ፤ የእረኞችም አለቃ በሚገለጥበት ጊዜ የማያልፈውን የክብርን አክሊል ትቀበላላችሁ። …”

 ግብረ ሐዋርያት፡– (ሐዋ. ፩፥፮)

“እነርሱም በተሰበሰቡ ጊዜ ጌታ ሆይ፥ በዚህ ወራት ለእስራኤል መንግሥትን ትመልሳለህን? ብለው ጠየቁት። እርሱም። አብ በገዛ ሥልጣኑ ያደረገውን ወራትንና ዘመናትን ታውቁ ዘንድ ለእናንተ አልተሰጣችሁም፤ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ አለ። ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው።”

ምስባክ፡– (መዝ. ፴፱፥፰)

ከመ እንግር ፈቃደከ መከርኩ አምላኪየ፤ ወሕግከኒ በማዕከለ ከርሥየ፤ ዜኖኩ ጽድቀከ በማኅበር ዐቢይ፡፡
ትርጉም፦ “አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፥ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው። በታላቅ ጉባኤ ጽድቅን አወራሁ፡፡”

 ወንጌል (ማቴ. ፳፭፥፲፬፴፩)

“መንገድ እንደሚሄድ አገልጋዮቹንም ጠርቶ ሊያተርፉበት ገንዘቡን እንደሰጣቸው ሰው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ችሎታው ለአንዱ አምስት፣ ለአንድ አምስት፣ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ያ አምስት መክሊት የተቀበለውም ሄደ፤ ነግዶም ሌላ አምስት መክሊት አተረፈ፡፡ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ወርቅ ቀበረ፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ተመልሶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና፡- አቤቱ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት አተረፍሁ፤ ብሎ አምስት መክሊት አስረከበ፡፡ ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም መጥቶ ፡- አቤቱ ሁለት መክሊትን ሰጥተኸኝ አልነበረምን? እነሆ ሌላ ሁለት መክሊትን አተረፍሁ አለ፡፡ ጌታውም፡- መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለውም መጣና እንዲህ አለ፡- አቤቱ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሄድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤ እንግዲህ እነሆ መክሊትህ፡፡ ጌታውም መልሶ አለው፡- አንተ ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እኔ ካልዘራሁበት የማጭድ ካልበተንሁበት የምሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንሁ ታውቃለህ? ገንዘቤን ለለዋጮች መስጠት በተገባህ ነበር፤ እኔም ራሴ መጠቼ ገንዘቤን ከትርፉ ጋር በወሰድሁ ነበር፡፡ የቆሙትንም እንዲህ አላቸው፡- ይህን መክሊት ከእርሱ ተቀብላችሁ ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ሁሉ ይሰጡታልና ይጨምሩለታልም፡ ለሌለው ግን ያንኑ ያለውን ይወስዱበታል፡፡ ክፉውን አገልጋይ ግን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት በውጭ ወደአለ ጨለማ አውጡት፡፡”

ቅዳሴ: ዘባስልዮስ

ደብረ ዘይት (የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት)

ደብረ ዘይት የቃሉን ፍቺ ስንመለከት ደብር ተራራ ማለት ሲሆን ዘይት” የሚለው ቃል ደግሞ ወይራ ማለት ነው። ስለዚህ ደብረ ዘይት በወይራ ዛፍ የተሸፈነ ተራራ ማለት ነው። 

ይህ የደብረ ዘይት ተራራ ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ በደብረ ቄድሮን ሸለቆ ብቻ አለ። ከታች ጌቴ ሴማኒ የተባለው የአትክልት ስፍራ ሲገኝ የጸሎተ ሐሙስ ማታ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተያዘበትና በኋላም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቅዱስ ሥጋዋ ረፈበት በዚህ ተራራ ግርጌ ነው። ቤተ ፋጌ እና ቢታንያ በኮረብታው ጫፍ እና በምሥራቅ ዳገታማ ቦታ ላይ ይገኛሉ። ይህ ተራራ በመጽሐፍ ቅዱስ በርካታ ድርጊቶች የተፈጸሙበት ቦታ ነው።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ቤተ መቅደሱ መፍረስ፣ ስለ ዓለም ፍጻሜና ስለ ዳግም ምጽአቱ የተናገረው በዚህ ተራራ ላይ ነው። ቀን ቀን በከተማና በገጠር ሲያስተምር ውሎ ሌሊት የሚያድርበት የኤሌዎን ዋሻም የሚገኝበት ነው፣ በዚሁ ተራራ ላይ ወደ ሰማይ ዐርጓል፣ ምጽአቱም በዚሁ ተራራ ላይ እንደሚገለጥ ትንቢት ተነግሯል። (ዘካ. ፲፬፥፫-፭)

አንድ ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ሲሄድ ደቀ መዛሙርቱም የቤተ መቅደሱን ሕንፃ አድንቀው አሠራሩን አያሳዩት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ አላቸው፡፡ “ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም፡፡” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም “ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የመመጣትህና የዓለሙ ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድነው?” አሉት፡፡

“የሚያስታችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና ብዙዎችንም ያስታሉ፡፡ ጦርነትን፣ የጦርነት ወሬም ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠንቀቁ፤ አትደንግጡ ነገር ግንፍጻሜው ገና ነው፡፡ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ፤ በየሀገሩም ረኃብና ቸነፈርም፣ የምድር መናወጥም ይሆናል፡፡ …” (ማቴ. ፳፬፥፩-ፍጻሜው) በማለት መለሰላቸው፡፡   

የዳግም ምጽአት ምልክቶች፦

. የሐሰተኞች ክርስቶሶች መምጣት (ራእ. ፲፫፥ ፭፣፳፫)

. ጦርነት (ማቴ. ፳፬፥፮)

. ረኃብ (ማቴ. ፳፬፥፯)

. የመሬት መንቀጥቀጥ (ማቴ. ፳፬፥፯)

. የክርስቲያኖች መከራ (ማቴ. ፳፬፥፱)

. የሐሰተኞች ነቢያት መምጣት (ማቴ. ፳፬፥፲፩፣፳፮)

. የፍቅር መጥፋት (ማቴ. ፳፬፥፲፪)

. የወንጌል ለዓለም መዳረስ (ማቴ. ፳፬፥፲፬)

የምጽአቱ ምሳሌዎች

ፍጥነቱ፦ ፈጥነቱ እንደ መብረቅ ነው። “መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፥ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይሆናል» (ማቴ. ፳፬፥፳፯) ተብሏልና።

ቀኑ አለመታዎቁ፦ እንደ ሌባ ነው። ያን ግን ዕወቁ፤ ባለቤት ከሌሊቱ በየትኛው ክፍል ሌባ እንዲሚመጣ ቢያውቅ ኖሮ፥ በነቃ ቤቱም ሊቈፈር ባልተወም ነበር … የሰው ልጅም በማታስቡበት ሰዓት ይመጣል (ማቴ. ፳፬፥፵፫-፵፬)።

ወቅታዊ መልእክቱ

ተጠንቀቁ፦ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ ((ማቴ. ፳፬፥፬)።

ንቁ፦ጌታችሁ በምን ሰዓት እንዲመጣ አታውቁምና እንግዲህ ንቁ ((ማቴ. ፳፬፥፵፪)

ተማሩ፣ ዕወቁ፦ እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ [ከላይ የተናገራቸውን ምልክቶች ሁሉ] ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ (ማቴ. ፳፬፥፴፫))።

አትደንግጡ፦ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፥ አትደንግጡ (ማቴ. ፳፬፥፮))

ትጉና ጸልዩ፦ ነገር ግን ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ (ማቴ. ፳፬፥፳)

ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፦ ስለዚህ እናንተ ደግሞ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፥ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና።((ማቴ. ፳፬፥፵፬)

ጽኑ፦ እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል (ማቴ. ፳፬፥፲፫)

በዚህች ደብረ ዘይት በተባለች ሳምንት እሑድ ጌታችን በዚህች ምድር ሲመላለስ የፈጸመውን ሥራ የሚያስረዱ የሚነበቡት ምንባባት የሚከተሉት ናቸው፡፡

መልዕክታት፡- (፩ኛ ተሰ. ፬፥፲፫-፲፰)

(፪ኛ ጴጥ. ፫፥፯-፲፭)

ግብረ ሐዋርያት፡- (ሐዋ. ፳፬፥፩-፳፪)

ምስባክ፡- (መዝ. ፵፱፥፪-፫)

“እግዚአብሔርሰ ገሀደ ይመጽእ፤

ወአምላክነሂ ኢያረምም፤

እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፡፡”

ትርጉም፡-

“እግዚአብሐር ግልጥ ሆኖ ይመጣል፤አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም፤

እሳቱ በፊቱ ይቃጠላል፡፡”

ወንጌል፡- (ማቴ. ፳፬፥፩-፳፮)

ቅዳሴ፡- ቅዳሴ አትናቴዎስ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ልትድን ትወዳለህን?”

በኢየሩሳሌም በበጎች በር አጠገብ አንዲት መጠመቂያ ነበረች፡፡ ይህች መጠመቂያም በእብራይስጥ ቤተ ሳይዳ ስትባል አምስት አርከኖች ነበሯት፡፡ በዚያም ዕውሮችና አንካሶች፣ ሰውነታቸው የሰለለ በርካታ ድውያን ተጠምቀው ይድኑ ዘንድ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ወንዙ ወርዶ ውኃውን እስኪያነዋውጠው ድረስ ይጠባበቁ ነበር፡፡ ውኃው በሚነዋወጥበት ጊዜም በመጀመሪያ ወርዶ የተጠመቀባት ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበር፡፡ (ዮ.፭፥፩-፬)

በዚህ ሥፍራ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ያህል ድኅነትን ሽቶ ከዛሬ ነገ እድናለሁ እያለ ይጠባበቅ የነበረ በሽተኛ (መጻጉዕ) ነበር፡፡ ሕሙማኑ በቤተ ሳይዳ መጠመቂያ የተሰበሰቡት ድኅነትን ፍለጋ ነው፡፡ ዛሬ ደዌ የጸናበት ከደዌ (ከበሽታ) ለመፈወስ ወደ ጠበል እንደሚሄድ በዘመነ ብሉይ የእግዚአብሔር መልአክ (ቅዱስ ሩፋኤል) በሳምንት አንድ ቀን ወደዚያች መጠመቂያ ገብቶ ውኃውን ሲያናውጥ ቀድሞ ወደ መጠመቂያይቱ የገባ ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበር፡፡ ዕለቷም ቀዳሚት ሰንበት (ሰንበተ አይሁድ) ነበረች፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በበሽታ ሲማቅቅ የነበረውን ሰው በዚያ በቤተ ሳዳ መጠመቂያው አጠገብ ተኝቶ አገኘው፡፡ የጠየቁትን የማይረሣ፣ የለመኑትን የማይነሣ አምላክ ነውና የመጻጉዕን ስቃይ ተመለከተ፡፡ ዝም ብሎም ያልፈው ዘንድ አልወደደም፡፡ ፈቃዱንም ይፈጽምለት ዘንድ “ልትድን ትወዳለህን?” ሲል ጠየቀው፡፡ በሽተኛውም “አዎን ጌታዬ ሆይ፤ ነገር ግን ውኃው በተናወጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም፤ እኔ በምመጣበት ጊዜ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል” አለው፡፡ (ዮሐ. ፭፥፮-፯) መጻጉዕ አጠገቡ ያለው ቆሞም በሐዘኔታ እየተመለከተ የሚጠይቀው ማን እንደሆነ አላወቀምና ለሠላሳ ስምንት ዘመናት ከአልጋው ጋር ተጣብቆ በሕመም ሲሰቃይ መኖሩን፣ እንደ ሌሎቹም በሽተኞች በፍጥነት ወደ መጠመቂያው መውረድ እንዳልቻለ ለማስረዳት ሞከረ፡፡

ጌታችን መድኃኒታቻን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃሉ ብቻ መፈወስ ይችላልና በቅፍርናሆም የመቶ አለቃው ልጅ በታመመ ጊዜ መቶ አለቃው በእምነት ሆኖ “አቤቱ አንተ ከቤቴ ጣራ በታች ልትገባ አይገባኝም፤ ነገር ግን በቃልህ እዘዝ፣ ልጄም ይድናል“ብሎ እንደጠየቀው “እንግዲህ ሂድ እንደ እምነትህ ይሁንልህ” ብሎ በዚያች ስዓት ልጁን እንዳዳነው መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ (ማቴ.፰፥፰) ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለመጻጉዕ በቅድሚያ ፈቃዱን ነው የጠየቀው፡፡ መጻጉዕም ከዚያ ሲያሰቃየው ከነበረው ደዌ መፈወስ ሽቷልና ምላሹ “አዎን ጌታዬ ሆይ” ነበር፡፡

መጻጉዕ በመጠመቂያው ዳር አልጋው ላይ ተጣብቆ ሳለ ከእርሱ በኋላ መጥተው ከእርሱ በፊት ድነው የሚሄዱ ሰዎች ሲመለከት ሠላሳ ስምንት ዓመታት አሳልፏል፡፡ ዓመቱ በረዘመ ቁጥር ተስፋ ቆርጦ ቤተ ሳይዳን ቤቴ ብሎ ከመኖር በስተቀር ምንም አማራጭ አልበረውም፡፡ በቤተ ሳይዳ መጠመቂያ ስፍራ አምስት መመላለሻዎች ማለትም፡- በሽተኞች፣ አንካሶች፣ ዕውሮችና እግራቸው የሰለለ ድኅትን ሽተው የአምላካቸው ማዳን ይጠባበቁ ነበር፡፡ በየሳምንቱም መልአኩ ከሰማይ ወርዶ ውኃውን ባናውጠው ጊዜ ቀድሞ የገባው አንድ ሰው ብቻ ይድናል፡፡ ይህንን ዕድል ለማግኘት ደግሞ መጻጉዕ አልታደለም፤ ለምን ቢሉ ሌሎች ቅድመውት ወደ መጠመቂያው ይወርዳሉ፡፡ እርሱም ብቻ አይደለም አንካሶች፣ ዕውሮችና እግራቸው የሰለለ ሰዎችም አቅሙ ስለማይኖራቸው ወደ መጠመቂያው ቢወርዱም በሌላው ስለሚቀደሙ ከውኃው የሚያወጣቸው አያገኙም፡፡ ስለዚህ ከውኃው መልሶ የሚያወጣቸው ሰው ያስፈልጋቸዋል፡፡

መጻጉዕ በዚህ ስፍራ የአንድ ጎልማሳ ዕድሜን ያህል ጊዜ እግዚአብሔርን ደጅ በመጥናት አሳልፏል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዚህን ሰው ችግር ያወቀው ማንም ሳይነግረው ነው፡፡ ይፈውሰውም ዘንድ ወደ እርሱ ቀርቦ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው፡፡ ጌታችን የሚፈልገው ይህንን ሰው መፈወስ እንጂ የራሱን ማንነት ማሳየት ስላልነበረ “ላድንህ ትወዳለህን?” አላለውም፡፡ ይህ ሰው የጌታችንን ማንነት አያውቅም፡፡ ነገር ግን ድኅነትን ናፍቋልና “ልትድን ትወዳለህን?” ባለው ጊዜ አላመነታም፡፡ “አዎን ጌታዬ ሆይ” ሲል መለሰ፡፡

ጌታችንምመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በሽተኛውን ይፈውሰው ዘንድ ፈቃዱ ስለሆነ ወደ መጠመቂያው ውረድ አላለውም፡፡ በተቃራኒው ጌታችን በቃል ብቻ መፈወስ ይችላላና “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ” አለው፡፡ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባላሰበው ባልጠበቀው መንገድ ፈወሰው፡፡ ይህ ሰው ሠላሳ ስምንት ዓመት ሙሉ ሲጠባበቃት የነበረችውን የቤተ ሳይዳ ጠበል ሳያገኝ ፣ በመልአኩ መውረድ ሳይሆን በመላእክት ፈጣሪ ቃል ተፈወሰ፡፡

ከላይ የመቶ አለቃውን ልጅ በቃል ብቻ እንደፈወሰው አይተናል፤ በተጨማሪም በጠበል ተጠምቆ መዳንን በተመለከተ ዕውር ሆኖ የተወለደውን ሰው ታሪክ ማንሣት እንችላለን፡፡ ዕውር ሆኖ በተወለደው ሰው ምክንያት ደቀ መዛሙርቱ “ይህ ሰው ዕውር ሆኖ የተወለደው በማን ኃጢአት ነው? በራሱ ነውን? ወይስ በወላጆቹ?” ብለው በጠየቁት ጊዜ “የእግዚአብሔር ሥራ ሊገለጥበት ነው እንጂ እርሱ አልበደለም፤ ወላጆቹም አልበደሉም፤ …” አላቸው፡፡ በዚህ ብቻ አላበቃም በምድር ላይ ምራቁን እንትፍ አለ፤ ምራቁንም ጭቃ አድርጎ የዕውሩን ዐይኖች ቀባው፡፡ እንዲህም አለው” ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ” አለው፤ ከቶ ለእግዚአብሔር የሚሣነው ነገር የለምና ዕውሩ በታዘዘው መሠረት ሄዶ ታጠበና እያየ ተመለሰ፡፡ (ዮሐ. ፱፥፩-፯) መጻጉዕንም ጠበል ሳያስፈልገው “አልጋህን ተሸክመህ ሂድ” ብሎታልና ተፈውሶ እርሱን ለሠላሳ ስምንት ዓመት ተሸክማው የነበረችውን አልጋ ተሸክሞ ለመሄድ በቃ፡፡

 በእነዚህ ታሪኮች እንደተመለከትነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ በወደደው መንገድ ማለትም፡- በጠበል፣ ያለ ጠበልም፤ በቃሉ፣ በዝምታ፣ በሌሎችም መንገዶች ማዳን እንደሚችል እንረዳለን፡፡ መጻጉዕንም ሳይውል ሳያድር፣ ላገግም ሳይል በቅጽበት አፈፍ ብሎ ተነሥቶ የተሸከመችውን አልጋ ተሸክሞ ለመሄድ ችሏል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን መሠረት አድርጋ የዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንትን “መጻጉዕ” ብላ ሰይማዋለች፡፡

ጌታችን መጻጉዕን ብቻ ፈውሶት ሔደ? ቢባል የፈወሰው እርሱን ብቻ አይደለም፡፡ እርሱን በሥጋ ቢፈውሰውም ተአምራቱን አይተው በማመናቸው በነፍሳቸው የተፈወሱ ይበዛሉ፡፡ “ሕሙማነ ሥጋን በተአምራት፣ ሕሙማነ ነፍስን በትምህርት እየፈወሰ” እንዲሉ አበው በዚያ ሥፍራ በሥጋ ታመው በነፍሳቸው አምነው የዳኑ ብዙዎች ናቸው፡፡

ይህ ሰው ተፈውሶ አልጋውን ተሸክሞ ሲሔድ ሰንበት ለሰው ድኅነት እንደተፈጠረች ያልተረዱ አይሁድ ከአልጋው ተነሥቶ የተሸከመችውን አልጋ ተሸክሞ በአደባባይ ሲያዩት በተሠራው የድኅነት ሥራ አልተደሰቱም፡፡ በዚህም ምክንያት “ዛሬ ሰንበት ነው፤ አልጋህን ልትሸከም አይገባህም” አሉት፡፡ “እንኳን ለዚህ አበቃህ!” ያለው ግን አንድም ሰው አልነበረም፡፡

መጻጉዕም መልሶ “ያዳነኝ እርሱ አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለኝ” አላቸው፡፡ አይሁድም አንድ ጊዜ ጠይቀው ብቻ አላለፉትም ያዳነውን “ሰንበትን ሽሯል” ብለው ለመክሰስ ፈልገዋልና  “አልጋህን ተሸክመህ ሂድ ያለህ ሰውዬው ማነው?” በማለት ጠየቁት፡፡ በወቅቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመካከላቸው ተሰውራቸዋልና በቦታው ሊያገኘው አልቻለም፡፡ ነገር ግን መጻጉዕ ያዳነውን ጌታችንን በቤተ መቅደስ አገኘውና ሄዶ ያዳነው ኢየሱስ እንደሆነ ለአይሁድ ነገራቸው፡፡

መጻጉዕ ከዚህ በኋላ ወደ አይሁድ ሄዶ ጌታን መክሰሱና ለጌታ ሞት የመማከራቸው ምክንያት መሆኑ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እነሆ ድነሃል፤ ግን ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ዳግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ” ብሎት ነበርና (ዮሐ. ፲፰፥፳፫) ነገር ግን ሊሰማው አልፈቀደም፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተያዘበት በምሴተ ሐሙስ ለሊቀ ካህናቱ አግዞ ጌታችንን በጥፊ መታው፡፡ “ወርቅ ላበደረ ጠጠር” እንዲሉ አበው የሠላሳ ስምንት ዓመት ስቃዩን ረስቶ፣ ከዚያ በላይ መከራ እንደሚያገኘው እየተነገረው ያዳነውን አምላኩን ካደ፡፡

ምንባባትና መልእክታት

የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት (ገላ. ÷ፍጻሜ)

“እንግዲህ ጸንታችሁ ቁሙ፤ እንደገናም በባርነት ቀንበር አትኑሩ፡፡ እነሆ÷እኔ ጳውሎስ እላችኋለሁ፤ “ብትገዘሩም በክርስቶስ ዘንድ ምንም አይጠቅማችሁም፡፡” ደግሞም ለተገዘረ ሰው ሁሉ የኦሪትን ሕግ መፈጸም እንደሚገባው እመሰክራለሁ፡፡  …” (ገላ. ፭÷፩-ፍጻሜ)

የቅዱስ ያዕቆብ መልእክት (ያዕ. ፭÷፲፬- ፍጻሜ)

“ከእናንተ የታመመ ሰው ቢኖር በቤተ ክርስቲያን ያሉ ቀሳውስትን ይጥራና ይጸልዩለት፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተጸለየበትንም ዘይት ይቅቡት፡፡ የሃይማኖት ጸሎትም ድውዩን ይፈውሰዋል፤ እግዚአብሔርም ያስነሣዋል፤ ኃጢአትንም ሠርቶ እንደሆነ ይሰረይለታል፡፡ …”  (ያዕ. ፭÷፲፬- ፍጻሜ)

ግብረ ሐዋርያት (የሐዋ÷፲፩)

“ጴጥሮስና ዮሐንስም በዘጠኝ ሰዓት ለጸሎት በአንድነት ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ፡፡ ከእናቱ ማኅፀንም ጀምሮ እግሩ ሽባ ሆኖ የተወለደ አንድ ሰው ነበር፤ ወደ መቅደስም ከሚገቡት ምጽዋት ይለምን ዘንድ ሁል ጊዜ እየተሸከሙ መልካም በሚሏት በመቅደስ ደጃፍ ያስቀምጡት ነበር፡፡ ጴጥሮስንና ዮሐንስንም ወደ መቅደስ ሲገቡ አይቶ ምጽዋት ይሰጡት ዘንድ ለመናቸው፡፡ ጴጥሮስም ከዮሐንስ ጋር ትኩር ብሎ ተመለከተውና “ወደ እኛ ተመልከት” አለው፡፡ ወደ እነርሱም ተመለከተ፤ ምጽዋት እንደሚሰጡትም ተስፋ አድርጎ ነበር፡፡ ጴጥሮስም “ወርቅና ብር የለኝም ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ እነሆ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሥተህ ሂድ” አለው፡፡ በቀኝ እጁም ይዞ አስነሣው፤ ያን ጊዜም እግሩና ቁርጭምጭሚቱ ጸና፡፡ …” (የሐዋ÷፲፩)

የዕለቱ ምስባክ (መዝ÷)

“እግዚአብሔር ይረድኦ ውስተ ዓራተ ሕማሙ፤

ወይመይጥ ሎቱ ኩሉ ምስካቤሁ እምደዌሁ

አንሰ እቤ እግዚኦ ተሣሃለኒ፤ እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ሳለ ይረዳዋል፤ መኝታውን ሁሉ በበሽታው ጊዜ ያነጥፍለታል፤ እኔስ አቤቱ ማረኝ።” (መዝ. ፵÷፫)

ወንጌል (ዮሐ፭፥፩፳፬)

“ከዚህ በኋላ የአይሁድ በዓል እንዲህ ሆነ፤ ጌታችን ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ። በኢየሩሳሌምም በበጎች በር አጠገብ መጠመቂያ ነበረች፤ ስምዋንም በዕብራይስጥ ቤተ ሳይዳ ይሉአታል፣ አምስት እርከኖችም ነበሩአት፡፡ በዚያም ዕውሮችና አንካሶች፣ ሰውነታቸውም የሰለለ ብዙ ድውያን ተኝተው የውኃውን መናወጥ ይጠባበቁ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ መጠመቂያው ወርዶ ውኃውን በሚያናውጠው ጊዜ ከውኃው መናወጥ በኋላ በመጀመሪያ ወርዶ የሚጠመቅ ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበርና፡፡ በዚያም ከታመመ ሠላሳ ስምንት ዓመት የሆነው አንድ ሰው ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስም በአልጋው ተኝቶ ባየ ጊዜ በደዌ ብዙ ዘመን እንደቆየ ዐውቆ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው፡፡ ድውዩም መልሶ “አዎን ጌታዬ ሆይ ነገር ግን ውኃው በተናወጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም፡፡ እኔ በምመጣበት ጊዜ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡ አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም “ተነሥና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ” አለው፡፡ ወዲያውኑም ያ ሰው ድኖ አልጋውን ተሸክሞ ሄደ፤ ያች ቀንም ሰንበት ነበረች፡፡ …” (ዮሐ.  ፥፩፳፬)

ቅዳሴ  ቅዳሴ ዘእግዚእነ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምኵራብ (የዐቢይ ጾም ሶስተኛ ሳምንት)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንትን ምኵራብ ብላ ትጠራዋለች። ምኵራብ ሰቀላ መሰል አዳራሽ፣ የአይሁድ የጸሎት ቤት ማለት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን አይሁድ በኢየሩሳሌም ሥርዓተ አምልኮ የሚፈጽሙበት ቤተ መቅደስ ነበር፡፡ ናቡከደነፆር ኢየሩሳሌምን    በመውረር ቤተ መቅደሳቸውን አፍርሶ ሕዝቡን ወደ ባቢሎን ካፈለሰ ጊዜ ጀምሮ አይሁድ በሚገኙባቸው ስፍራዎች ሁሉ ለጸሎት ምኵራብ መሥራት እንደ ጀመሩ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላትይገልጻል፡፡

አይሁድ በምኲራቦቻቸው የሕግና የነቢያት መጻሕፍትን (የብራና ጥቅሎች) በአንድ ሣጥን ውስጥ በማስቀመጥ የጸሎት ስፍራዎቻቸውን ለትምህርትና ለአምልኮ ይጠቀሙባቸዋል፡፡ በዓመት አንድ ጊዜ የሚቀርበውን መሥዋዕትና መባዓ ለመስጠትም ወደ ቤተ መቅደስ ይወጡ ነበር፡፡ ይህንን መሠረት አድርጎም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ኦሪትንና ነቢያትን ልሽራቸው የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ ልፈጽማቸው እንጂ ልሽራቸው አመልመጣሁም፡፡” እንዲል ሕግ ሊፈጽም ወደ ቤተ መቅደስ ይሄድ ነበር፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ መሄድ ብቻ ሳይሆን በምኵራብ እየተገኘም ያስተምር ነበር፡፡ “ዕለት ዕለትም በቤተ መቅደስ ያስተምር ነበር፡፡” (ሉቃ. ፲፱፥፵፯)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኵራብ ተገኝቶ በሚያስተምርበት ወቅት ነጋዴዎች በመሸጥና በመለወጥ ቤተ መቅደሱን ያውኩ ስለነበር ቤተ መቅደሱን ለማስከበር ሲል በዚያ ያሉትን ሻጮችንና ለዋጮችን እየገረፈ፣ የሚሸጡትንም እየገለበጠ አስወጥቷቸዋል፡፡ “ኢትግበሩ ቤተ አቡየ ቤተ ምሥያጥ፤ ቤትየሰ ቤተ ጸሎት ይሰመይ፤ ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል ተብሎ ተጽፎአል፤ እናንተ ግን የሌባና የቀማኛ ዋሻ አደረጋችሁት” አላቸው፡፡ በዚህ ብቻ አላበቃም “በቤተ መቅደስም በሬዎችና በጎችን፣ ርግቦችን የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ። የገመድም ጅራፍ አበጀ፤ በጎችንና በሬዎችን ሁሉንም ከቤተ መቅደስ አስወጣ፤ የለዋጮችንም ገንዘብ በተነ፣ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ። ርግብ ሻጮችንም ‘ይህን ከዚህ አውጡ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉ፡፡” በማለት አስወጣቸው፡፡ (ዮሐ. ፪፥፲፬-፲፮) በዚህም መሠረት የዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንት ምኵራብ ተብሏል፡፡

ዛሬም በዘመናችን የእግዚአብሔርን የቅድስና ስፍራ የሚዳፈሩ፣ ለሙስና እና ለራስ ወዳድነት ያደሩ ከአገልጋዮች እስከ ምእመናን ድረስ እንዳሉ ይታወቃል፡፡ በደሙ የዋጃትን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ‘የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት’ እያለ ዛሬም የእግዚአብሔር ድምፅ ይጣራል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በዘር፣ በጎሳ፣ በቋንቋ፣ በመንደር፣ … በመከፋፈል ለቃለ እግዚአብሔር ባለመታመን ኃጢአት የምንሠራና የግል ፍላጎታችንን ለማሟላት የምንሮጥ ብዙዎች ነን፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖና፣ ሥርዓትና ትውፊት በመጠበቅ በንስሓ ሕይወት በመመላለስ ከማገልገል ይልቅ ግላዊ ፍላጎትን ለማሟላት የምንሮጥ ሁሉ ራሳችንን መመርመር፣ ከክፉ ተግባራችንም መመለስ ይጠበቅብናል፡፡ ይህ ካልሆነ እግዚአብሔር ምሕረቱ የበዛ አምላክ እንደ መሆኑ መጠን ክፉ ሥራችን በበዛ ቁጥር የቁጣ በትሩን ማሳረፉ አይቀርምና በዚህ በዐቢይ ጾም በተሰበረ ልብ ሆነን በይቅርታው ይጎበኘን ዘንድ ዘወትር ያለመታከት ልንማጸን፣ ልንጸልይ ይገባል፡፡

በዕለቱ የሚነበቡ መልእክታት፣ ምስባክ እና ወንጌል

መልእክታት፡–  

የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት፡ “እንግዲህ በመብልም ቢሆን በመጠጥም ቢሆን በልዩ ልዩ በዓላትም ቢሆን በመባቻም ቢሆን በሰንበትም ቢሆን የሚነቅፋችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፡፡ ይህ ሁሉ ይመጣ ዘንድ ላለው ጥላ ነውና፤ አካሉ ግን የክርስቶስ ነው፡፡ በመታለልና ራስን ዝቅ በማድረግ ለመላእክት አምልኮ ትታዘዙ ዘንድ ወድዶ በአላየውም በከንቱ የሥጋው ምክር እየተመካ የሚያሰንፋችሁ አይኑር፡፡ ሥጋ ሁሉ ጸንቶ በሚኖርበት በሥርና በጅማትም በሚስማማበት በእግዚአብሔርም በሚያድግበትና በሚጸናበት፣ በሚሞላበትም በራስ አይጸናም፡፡

ከዚህ ዓለም ኑሮ ከክርስቶስ ጋር ከሞታችሁ እንደገና በዓለም እንደሚኖሩ ሰዎች እንዴት ትሠራላችሁ? እንዴትስ ይህን አትዳስስ፣ ይህን አትንካ፣ ይህንም አትቅመስ፣ ይሉአችኋል? ይህ ሁሉ እንደ ሰው ትእዛዝና ትምህርት ለጥፋት ነውና፡፡ ይህም ስለ ልብ ትሕትናና እግዚአብሔርንም ስለ መፍራት፣ ለሥጋም ስለ አለማዘን ጥበብን ይመስላል፤ ነገር ግን ከሥጋ በላይ ነው እንጂ ምንም ክብር የለውም፡፡” (ቆላስ. ፪፥፲፮-፳፫)

የቅዱስ ያዕቆብ መልእክት፡ “ወንድሞቼ ሆይ፣ እምነት አለኝ ምግባር ግን የለኝም የሚል ሰው ቢኖር ምን ይጠቅመዋል? በውኑ እምነቱ ልታድነው ትችላለችን? ከወንድሞቻችን ወይም ከእኅቶቻችን የታረዙ ወይም የዕለት ምግብ ያጡ ቢኖሩ ከእናንተም አንዱ ‘በሰላም ሂዱ እሳት ሙቁ ትጠግባላችሁም’ ቢላቸው ለችግራቸውም የሚሹትን ባይሰጣቸው ምን ይጠቅማቸዋል? እንዲሁም ሥራ የሌለው እምነት ቢኖር በራሱ የሞተ ነው፡፡

ነገር ግን አንድ ሰው “አንተ እምነት አለህ እኔም መልካም ሥራ አለኝ፤ እስቲ ሃይማኖትህን ከሥራህ ለይተህ አሳየኝ፤ እኔም እምነቴን በሥራዬ አሳይሃለሁ” ይላል፡፡ አንተም እግዚአብሔር አንድ እንደሆነ ታምናለህ፤ መልካምም ታደርጋለህ፤ እንዲህስ አጋንንትም ያምናሉ፤ ይንቀጠቀጣሉም፡፡ አንተ ሰነፍ ሰው እምነት ያለ ምግባር የሞተች እንደሆነች ልታውቅ ትወዳለህን? አባታችን አብርሃም ልጁን ይስሐቅን ወደ መሠዊያው ባቀረበው ጊዜ በሥራው የጸደቀ አይደለምን? እምነት ለሥራው ትረዳው እንደ ነበር፣ በሥራውም እምነቱ እንደመላችና ፍጽምት እንደሆነችም ታያለህን? መጽሐፍ አብርሃም በእግዚአብሔር አመነ፣ ጽድቅ ሆኖም ተቆጠረለት” የሚለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ፡፡ ሰው በሥራ እንደሚጸድቅ በእምነት ብቻ እንዳይደለ ታያለህን? እንዲሁ ዘማይቱ ረአብ ደግሞ ጉበኞችን ተቀብላ በሌላ መንገድ ባወጣቻቸው ጊዜ በሥራ አልጸደቀችምን? ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደሆነ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው፡፡” (ያዕ. ፪፥፲፬-፳፮)

የሐዋርያት ሥራ፡ “በቂሳርያም ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ ኢጣሊቄ ለሚሉት ጭፍራ የመቶ አለቃ ነበር፡፡ እርሱም ጻድቅና ከቤተሰቡ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነበር፤ ለሕዝብም ብዙ ምጽዋት ይሰጥ ነበር፤ ዘወትርም ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክም በራእይ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በግልጥ ታየው፤ ወደ እርሱም ገብቶ፡- “ቆርኔሌዎስ ሆይ” አለው፡፡ ወደ እርሱም ተመልክቶ ፈራና “አቤቱ ምንድነው?” አለ፤ መልአኩም እንዲህ አለው፡- “ጸሎትህም ምጽዋትህም መልካም መታሰቢያ ሆኖ ወደ እግዚአብሔር ዐርጓል፡፡ አሁንም ጴጥሮስ የሚባለውን ስምዖንን ይጠሩልህ ዘንድ ወደ ኢዮጴ ከተማ ሰዎችን ላክ፡፡ እርሱም ቤቱ በባሕር አጠገብ ባለው በቁርበት ፋቂው በስምዖን ቤት በእንግድነት ተቀምጧል፡፡ ልታደርገው የሚገባህን እርሱ ይነግርሃል፡፡” ያነጋገረውም መልአክ ከሄደ በኋላ ከሎሌዎቹ ሁለት፣ ከማይለዩት ጭፍሮቹም አንድ ደግ ወታደር ጠራ፡፡ ነገሩንም ሁሉ ነግሮ ወደ ኢዮጴ ከተማ ላካቸው፡፡” (የሐዋ. ፲፥፩-፱)

የዕለቱ ወንጌል

የዮሐንስ ወንጌል፡ “ከዚህም በኋላ እርሱና እናቱ ከወንድሞቹና ደቀ መዛሙርቱም ጋር ወደ ቅፍርናሆም ወረዱ፤ በዚያም ብዙ ያይደለ ጥቂት ቀን ተቀመጡ፡፡ የአይሁድም የፋሲካቸው በዓል ቀርቦ ነበር፤ ጌታችን ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፡፡ በቤተ መቅደስም በሬዎችንና በጎችን፣ ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፡፡ የገመድም ጅራፍ አበጀ፤ በጎችንና በሬዎችን፣ ሁሉንም ከቤተ መቅደስ አስወጣ፣ የለዋጮችንም ገንዘብ በተነ፣ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ፡፡ ርግብ ሻጪዎችንም “ይህን ከዚህ አውጡ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉ” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም “የቤትህ ቅናት በላኝ” የሚል ቃል ተጽፎ እንዳለ ዐሰቡ፡፡ …” (ዮሐ. ፪፥፲፪-፳፭)

ቅዳሴ

  • ቅዳሴ ዘእግዚእ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቅድስት (የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት)

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በጾመ ድጓ ድርሰቱ በዐቢይ ጾም ለሚገኙት ሳምንታት ማለትም በየሳምንቱ ለሚውሉት እሑዶች መዝሙር አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ በዚህም መሠረት እያንዳንዱ እሑድ በመዝሙሩ ስም ይጠራል። ባለፈው ሳምንት “ዘወረደ”ን እንዳቀረብን ሁሉ በዚህ ዝግጅታችን ደግሞ ሁለተኛውን ሳምንት ቅድስትን እንመለከታለን፡፡ ፡፡

የዐቢይ ጾም ሁለተኛው እሑድ ቅድስት ተብሎ ተሰይሟል። ቅድስት የሚለው ቃል ግሱ “ቀደሰ” ሲሆን “ለየ፣ አከበረ፣ መረጠ የሚል ትርጉም ሲኖረው፤- ቅድስት ማለት የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ማለት ነው። ቅዱስ የሚለው ቃል እንደ የአገባቡ ለፈጣሪም ለፍጡርም ያገለግላል። ለፈጣሪ ሲነገር እንደ ፈጣሪነቱ ትርጉሙ ይሰፋል፣ ይጠልቃል፡፡ ለፍጡር ሲነገር ደግሞ ቅድስናውን ያገኙት ከራሱ ከእግዚአብሔር ነው፡፡ “ያዘጋጃቸውን እነርሱን ጠራ፤ የጠራቸውንም እነርሱን አጸደቀ፤ የአጸደቃቸውንም እነርሱን አከበረ፡፡” እንዲል፡፡ (ሮሜ. ፰፥፴)

ዕለተ ሰንበት ቅድስት መባሏ በሰዎች እና በእግዚአብሔር መካከል ለቅድስና ሕይወት ምልክት ማስታወሻ እንድትሆን ነው። በባሕሪይው ቅዱስ የሆነ አምላክ ዓለምን የማዳን ሥራውን የጀመረበትን፣ ፅንሰቱን፣ እንዲሁም የማዳን ሥራውንም አጠናቆ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ዘለዓለማዊ ሕይወትን ያበሰረበትን ትንሣኤውን የምናስብበት በመሆኑ የዕለቱ ቅድስና፣ የፈጣሪን ቅዱስ ተግባር የምናደንቅበት፣ የዋለልንን ውለታ ከፍ ከፍ እያድረግን እርሱን የምናመሰግንበት ዕለት ነው። ይህም እኛን ወደ በለጠ የቅድስና ሕይወት የሚያሸጋግረን በመሆኑ የእግዚአብሔርን ጥልቅ ፍቅር በየጊዜው እንድናስብና በፍቅሩም እንድንኖር ያግዘናል፡፡

ዕለተ ሰንበት ነገረ እግዚአብሔር በተለየ ሁኔታ የሚዘከርባት ናትና “የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ” (ዘፀ. ፳፥፰) ተብሏል፡፡ የሰንበትን ቀን አስቀድሞ የቀደሰ፣ የባረከ ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ “እግዚአብሔርም ሰባተኛውን ቀን ባረከው፣ ቀደሰውም፤ እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ ዐርፎአልና“እንዲል፡፡ (ዘፍ. ፪፥፫)

“እንግዲህ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ”የተባለው እግዚአብሔር አስቀድሞ የባረከውን የቀደሰውን እኛ ድጋሚ የምንቀድስ የምንባርክ ሆነን ሳይሆን በዕለተ ሰንበት ራሳችንን በተለየ ሁኔታ ለቅዱስ ተግባር እንድንለይ፣ ለሥጋችን ከምንፈጽማቸው ተግባራት ይልቅ ለተግባረ ነፍስ እንድናደላ ያስረዳናል። ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት፤ ሐሤትን እናድርግ፥ በእርስዋም ደስ ይበለን።እንዳለው (መዝ. ፻፲፯፥፳፬)

በዕለተ ሰንበት የምእመናን መንፈሳዊ ሕይወት ይባረካል፣ ይቀደሳል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ “አንቀጸ ብፁዓን” በመባል የተጠቀሱትን መፈጸም ለክርስቲያን ሁሉ ይገባል፡፡ (ማቴ. ፭፥፩-፲፪) በዚህ ታሳቢነት ዕለቱም ዕለተ ቅድስና መሆኑን ለማጠየቅ ቅድስት ተብሏል። እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ (ዘሌ. ፲፱፥፪) ተብለናልና ቅድስት በተባለች ዕለተ ሰንበት ወደ ቤተ ክርስቲያን በመገስገስ ቅዳሴ በማስቀደስ፣ ቃለ እግዚአብሔር በመስማት፣ የታመመን፣ የታሠረን በመጠየቅ፣ በአጠቃላይ የቅድስና ሥራዎችን እንድንሠራ ለእኛ ለክርስቲያኖች ታዘናልና ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ የቅድስና ሕይወት መሠረቱ የእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ መጠበቅና ማድረግ ሆኖ ሳለ ለመቀደስ የእኛ መሻት፣ መፈለግ ወሳኝ ነው።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የግቢ ጉባኤያት ፲፫ኛው ዓለም አቀፍ ሴሚናር ሁለተኛ ቀን ውሎ

የማኅበረ ቅዱሳን ፲፫ኛውን ዓለም አቀፍ የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ሁለተኛ ቀን ውሎውን በጸሎት ተጀምሮ የቀጠለ ሲሆን በደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ስምዐ ጽድቅ ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበው በመ/ር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ “ለራሳችሁ አይደላችሁም” ፩ኛቆሮ. ፮፥፲፱-፳) በሚል የወንጌል ቃል መነሻነት የዕለቱን የወንጌል ትምህርት በመስጠት ቀጥሏል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የሆኑት አቶ ካሳሁን ኃይለ ማርያም በሴሚናሩ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልእክት “በኃላፊነት የምንማረው መንፈሳዊ ሕይወታችንን በእግዚአብሔር ቃል አንጸን እንድንኖር ነው፡፡ በመንፈሳዊም በሥጋዊም ሕይወታችሁ ይህንን ዓለም በማሸነፍ ለእናንተ ብቻ ሳይሆን ወንድሞቻችሁና እኅቶቻችሁም በትምህርታቸው በርትተው ለሀገርም ለቤተ ክርስቲያንም የሚጠቅሙ ሆነው እንዲወጡና ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ማገዝ ይጠበቅባችኋል፡፡ ይህንን መሰባበሰብና አንድነት የሰጠን እግዚአብሔር ነውና በጥንቃቄ ተምራችሁ ሕይወታችሁን እንድትመሩ፣ ከራሳችሁ አልፋችሁ ቤተ ክርስቲያንን እንድታገለግሉ ይገባል፡፡ ችግር ፈቺም ሆናችሁ የበኩላችሁን ኃላፊነት እንድትወጡና እንድታግዙ አደራ ማለት እፈልጋለሁ” ብለዋል፡፡  

በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት ቀጥሎ የቀረበው የግቢ ጉባኤያት መምህራን ማፍሪያ ፕሮጀክት የተመለከተ ሲሆን በ፲፫ኛው ዓለም አቀፍ የግቢ ጉባኤ ሴሚናር አዘጋጅ ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ በሆኑት በአቶ ዳንኤል ተስፋዬ እና  በሓጋዚ አብርሃ በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የአቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል ም/ኃላፊ ቀርቧል፡፡ በቀረበውም ጥናት በርካታ ጉዳዮች የተነሡ ሲሆን፡- የፕሮጀክቱ ዓላማ፣ የፕሮጀክቱ አስፈላጊነት፣ የፕሮጀክቱ ወሰን፣ የፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ ስልት፣ የፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ በጀት፣ የበጀቱ ምንጭ፣ የፕሮጀክቱ ትግበራ እና የፕሮጀክቱ ክትትልና ግምገማ ያካተተ ጥናት ቀርቧል፡፡ በቀረበው ጥናት መሠረትም ከተሳታፊዎች አስተያት እና ጥያቄዎች ቀርበው ማብራሪያ ተሰጥቶባቸው ጸድቋል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎችና የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት የተሰኘው ጥናት በሴሚናሩ ላይ ከቀረቡ መርሐ ግብሮች አንዱ ነበር፡፡ ጥናቱን ያቀረቡት አቶ አማረ በፍቃዱ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር አባል ሲሆኑ በጥናታቸውም ዘመናዊነት፣ የሉላዊነት መስፋፈት፣ በሃይማኖትና ሃይማኖተኝነት እያሳደረ ያለው ተጽእኖ፣ ዓለም ለሃይማኖት የሚሰጠው ዋጋ ዝቅ እያለ መሄዱ፣ የአስተሳሳብ ዘይቤ እየተዛባ መምጣቱ፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ህልውና ላይ እያሳደረ ያለው ተጽእኖ፣ በፖለቲካ፣ በብሔር፣ … በመከፋፈል የትርክት ሰለባ ማድረግ፣ ኢ-ኦርዶክሳዊነትን ከፍ ማድረግ፣ … የመሳሰሉትን በማንሣት ሰፊ ጥናት አቅርበዋል፡፡ ባቀረቡት ጥናት ላይ በመመርኮዝም ከተሳታፊዎች አስተያየት እንዲሁም ጥያቄዎች ተነሥተው ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

የቀኑ መርሐ ግብር ከመጠናቀቁ በፊት ዶ/ር ወርቁ ደጀኔ፣ ወ/ሮ የሱነሽ ተሾመ እና ዶ/ር ዲ/ን መገርሣ ዓለሙ የሕይወት ተሞክሯቸውን አካፍለው የሴሚናሩ ተሳታፊዎች የማኅበረ ቅዱሳን ብሮድካስት ተቋምንና የልማት ተቋማትን ኅትመት ክፍል ጎኝተዋል፡፡ በመጨረሻም ማምሻውን ለተሳታፊዎች ዘጋቢ ፊልም (ዶክመንተሪ) ቀርቦ በመ/ር ዋሲሁን በላይ በማኅበረ ቅዱሳን ዋና ሥራ አስፈጻሚ፣ በአቶ አበበ በዳዳ በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ሥራ አስፈጻሚ እና በሴሚናሩ አዘጋጅ ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ በአቶ ዳንኤል ተስፋዬ መልእክት የሴሚናሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡