ረቡዕ

ከመምህር ተሾመ ግዛው

እያንዳንዱ የሰሙነ ሕማማት ዕለታት ስያሜ እንዳላቸው ዕለተ ረቡዕም ራሱን የቸለ ምሥጢራዊና ታሪካዊ ትርጒም አለው፡፡ ይህም እንደሚከተለው በዝርዝርእንመለከታለን።
የምክር ቀን (ምክረ አይሁድ)
አይሁድ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስሰ ክርስቶስን የሚይዙበትን መንገድ ይፈልጉ ነበር፤ በመካከላቸው ምንም ዓይነት ልዩነት እንኳን ቢኖር ለኃጢአት ሥራ ግን ተባበሩ፡፡ ፰ት ለተለያየ አላማ የተቋቋመ ማኅበር (ስምንቱ ቤተ አይሁድ) ፦ ሊቃነ ካህናት፣ መገብተ ምኲራብ፣ ኃጥኣን መጸብሓን፣ ጸሓፍት ፈሪሳውያን፣ ሰዱቃውያን፣ ረበናት (መጽሓፈ ሰዓታት ንባቡና ትርጓሜው ሮዳስ ታደሰ ገጽ ፬፻፸፭)
ረበናት የሕዝቡን ሃይማኖታዊና ባሕላዊ ዕሤት ይጠብቃሉ ተብለው የተሾሙ ነበሩ፤ ነገር ግን ሕዝቡን ከመጥቀም ይልቅ የሚጎዳ ተግባር ላይ ተጠመዱ፤ ንጉስ ክርሰቶስን ለመስቀል በእለተ ረቡዕ ተማከሩ፤ ደሙም በላያቸው ላይ እንዲሆን በራሳቸው ላይ የሞት ፍርድን ፈረዱ። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እንደ ገለጸው ‹‹ማኀበራነ አይሁድ ተመድበሉ ለሰቂለ አምላክ ተማሐሉ፣ የአይሁድ ማኅበራት ተሰባሰቡ አምላክን ለመስቀል ተማማሉ›› ይች ዕለት የአዳም የመዳን ተስፋ፣ የነቢያት ትንቢታቸው ፍጻሜ እንዲያገኝ በቤተ አይሁድ ምክር የጸናበት እንዲሁም ለጨለማ አበጋዞች የኀዘን ዳራ የሰፋበት ነው፡፡
በዚህ ዕለት ጌታ ለሞት ተላልፎ እንዲሰጥ አይሁድ መክረው የተነሱበት አንዲሁም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእጃቸው የሚወድቅበት መንገድ ከይሁዳ ጋር ዘዴ የዘየዱበት ዕለት በመሆኑ የቤተ ክርስቲያነችን ሊቃውንት ዕለቱ ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዐመቱን ሙሉ በጾም እንዲታሰብ ሠርዓት ሠርተዋል።
የንስሓ ዕለት
ንስሓ ለሰው ልጅ ከበድል የሚነጻበት የነፍስ ሳሙና ነው፡፡ ቅዱሰ ኤፍሬም ሰለንስሓ እንዲህ ይለናል ‹‹ጌታ ሆይ ወርቅ ትሰጠኝ ዘንድ አለምንህም ወርቅ ክፉዎች የሚፈልጉት ንዋይ ነውና፡፡ ሀብትና ንብረትም አልለምንህም፤ እነርሱም ድኅነትን የሚያስገኙ አይደሉም፡፡ ይቅርታን ማግኘት ከወርቅ ይልቃል፡፡››
ጌታቾን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሠራቸው ድንቅ ሥራዎች ቅዱስ መጽሐፍ ማርያም ባለ ሽቶዋ በሚንቋትና ኃጢአተኛነቷን በየሄዱበት በሚመሰክሩባት ሴት ይቅርታን ያደረገበት ቀን ነው፡፡
ከቀናት ሁሉ ቅዱስ ተብለው የሚጠሩ ዕለታት ነፍስና ሥጋን የሚያነጹ ልዩ ዕለታቶች አሉ፡፡ ማርያም ለንስሓ የተነሳችበት ዕለት ከሌላው ጊዜ በተለየ ሁኔታ በኀዘንና በትካዜ የውስጧን ማንነት የሚያሳያትን በዓይነ ኅሊና ፊት እንጅ ለኃጢአትና ለበደል በሚያቆማት መስታወት ፊት ብቻ አልነበርም፡፡
ከዓይነ ሥጋ ዕይታ በመውጣት በዓይነ ኅሊና የታያት የክብር ዙፋን በመናፈቅ ውድና ክቡር የሆነ ሽቱ ፍለጋ ነበር የወጣችው፤ በወጣችበት ጊዜም ቀላል የማይባል ፈተና ገጥሟት ነበር፡፡ እርሱን ተቋቍማ ነገሥታት ይቀቡት የነበረውን እጅግ የከበረ ልዩ ሽቱ ፍለጋ ተንከራተተች፤ ፈልጋም ባገኘች ጊዜ በውድ ገንዘብ ገዛችው፡፡
የሽቱ ታሪክ በቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ይተረካል፡-
ሰባ ሰገል ለሕጻኑ የገበሩት ከጥንት አባቶቻቸው የመጣ ታሪክ እንዳለው ሁሉ ሽቱውም ልዩ ታሪክ አለው፡፡ ዳዊትና ሰሎሞን ይቀቡት የነበረዉ ውድ ሽቱ ሳይሆን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በወርኀ ስደቷ ጥጦስና ዳክርስ የተባሉ ሽፍቶች ነበሩ፤ እነዚህ ሽፍቶች የሕጻኑን ልብስና ጨማ ከዘረፉ በኋላ ፈያታዊ ዘየማን ሕጻኑን በመታቀፍ ሸኝቶት ነበር፤ የሕጻኑ ወዝም በሽፍታው ልብስ ይቀራል፤ ልዩ ጠረንም ነበረው፤ እንድታጥብለትም ለእናቱ ሲሰጣት ሽታው እስካሁን ከምታውቀው ሽቱ ሁሉ የተለየና በአንድ ተራ ሰው ቤት ሊገኝ የማገባው መሆኑን አውቃ ለነጋዴ ሸጠችው፤ ያ ነጋዴም የሚገዛው ሰው እስኪያገኝ ድረስ በልዩ ቦታ አስቀምጦት ነበር፤ ማርያም እንተ ዕፍረት በመጣች ጊዜ በውድ ዋጋ ሸጠላት፡፡
ማርያም እንተ ዕፍረት ይህንን የገዛችው ሽቱ ለክርሰቶስ እንዲገባ ዐውቃ የስምዖንን ዛቻና ግፊት ሳይበግራት በጽናት ተቋቍማ ወደ ክርስቶስ ቀርባ በፊቱ አቀረበችለት፡፡ በዐይኖቿም ዕንባ አፍሳ እግሮቹን አጠበችው፤ በዕንባዋ ያጠበችው እግሮቹም በጨርቅ ሳይሆን በውብ ፀጉሮቿ ነው እግሮቹን ያበሰችው፡፡
ያን ጊዜ ማርያም እንተ ዕፍረት በጌታ ዘንድ ከእንባዋ የተነሳ ይቅርታን አገኘች፤ ከበደል እስራትም ተፈታች፤ ከ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስትም ተቆጠረች፤ በቅዱሱ ዕለትም ቅድስናን ተቀበለች፡፡ (ሉቃ. ፯፥፴፯-፶)
ማርያም እንተ ዕፍረት እግዚብሔር የሰጣትን ውበትና መልክ ለቅድስና ሳይሆን ለኃጢአት አውላው ነበርና፤ ብዙዎቹ በእርሷ ውበት ተማርከው ገንዘባቸውን ጨረሱ፤ ትዳራቸውን አፈረሱ፤ ክቡር የሆነውንም የክርስቶስ ቤተ መቅደስ አረከሱ፤ በኃጢአት ዓለም እራሳቸውን አዋረዱ፤ ማርያም ግን ከዚህ ሁሉ ጥፋትና በደል በኋላ ወደ ቀልቧ ተመለሰች፤ ሁሉም ከንቱ መሆኑና በሚያልፈው ዓለም የማያልፈውን ክብር መግዛት ፈለገች፡፡
በማርያም እንተ ዕፍረት የሚከተሉትን የሕይወት ለውጥ እንመለከታለን፡-
ለኃጢአት ትጠቀመው የነበረውን መስታወት ለጽድቅ ማያ አደረገቸው፤
ለዝሙት ይውሉ የነበሩ ልብሶቿ ለክብር ሆኑ፤
ለዝሙት ይዘረጉ የነበሩ እጆች ለጽድቅ ተዘረጉ፤
ለዝሙት ይንበረከኩ የነበሩ እግሮቿ ለስግደት ተንበረከኩ፤
የጎልማሳ ቀልብን ሰብረው በመንገድ የሚያስቀሩ ዓይኖቿ የንስሓ እንባን አነቡ፤
ወደ ኃጢአት የእራት ግብዣ የሚገሰግሱ እግሮቿ ለክብር እንግድነት በቅድስና የእራት ግብዣ ቦታ ገሰገሱ፤
የጎልማሶች እጅ መንሻ በምትቀበልበት እጆቿ የተለየ ሽቱ ለነገሥታት እንደሚገባው ንጉሠ ነገሥት ለሆነው ለክርስቶስ አቀረበች፡፡
ይህች ዕለት ለእርሷ የተቀደሰ ሐሳብን ያሰበችበት፣ ያባከነችውን ጊዜ የምትክስበት፣ ለኃጢአት መኳኳል ትጠቀምበት የነበረውን ጊዜ ለጽድቅ ያደረገችበት ቅዱስ ዕለት፤ ከዓለም ሁካታና ጩኸት የተለየችበት ቅድስት እለት ናት፡፡
ዛሬ እኛ ከነበርንበት ውደቀት ለመውጣት ብዙ ምክንያች እንደረድራለን ያለንበትን ቦታና በዙሪያችን ያሉ ሰዎችን ከውደቀታችንም ላለመነሳት ምክንያት እናደርጋቸዋለን፡፡ ከዚህች ብርቱና ቆራጥ ሴት የምንማረው ለበጎ ተግባር ቁርጥ ውሳኔ መወሰንና ፈጥኖ በተግባር ማዋልን ነው። ያኔ ታላቅ የሕይወት ለውጥ በኑሯችን ይከሰታል።
ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን

ሰሙነ ሕማማት ሠሉስ

ከመምህር ተፈሪ መንገሻ

በኢ.ኦ.ተ.ቤ/ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት የሰሙነ ሕማማት ዕለታት የየራሳቸው ስያሜና ምሥጢር አላቸው። ከእነዚያ መካከል ዕለተ ሠሉስ የትምህርት ቀን የጥያቄ ቀን በመባል ይታወቃል።

ይህንንም አስመልክቶ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በዕለቱ ጌታ ረጅም ትምህርት ያስተማረበትና ከአይሁድ፣ ከጸሓፍትና ከፈሪሳውያን ብዙ የተንኮል ጥያቄዎችን ተቀብሎ ለእነርሱም በጥበብ መልስ የሰጠበትን ድንቅ ትምህርት ሥርዓት ሠርታ ትዘክራለች/ታስታውሳለች። ይህች ዕለት የሰው ልጅ ውሱን በሆነው አዕምሮውና በተንኮል በተሞላው ልቡ ጥበብንና እውነትን (ክርስቶስን) ሊፈትን የሞከረበትና ጥበብ ክርስቶስ ግን ጥያቄአቸውን በጥያቄ የረታበት፣ ሐሰታቸውን የገለጠበት ዕለት ነው።

በሰኞ ዕለት ነጋዴዎችን ከቤተ መቅደሱ በማስወጣት ስላነጻ፣ ስለገሠጸ በማግሥቱ ማክሰኞ ዕለት ይህንን በማን ሥልጣን እንደሚያደርገውና ሌሎች ብዙ ጥያቄዎችን ጠይቀውታል። (ሉቃ. ፲፥፵፭)

በእነዚህ ጥያቄዎች ውስጥ ብዙ ጥልቅ ምሥጢራትን የያዘ ክፍል ነውና እነርሱን በዝርዝር ከፋፍለን እንደሚከተለው እንዳስሳቸዋለን።

ተንኮል በጥበብ ፊት (ሉቃ. ፳፥፩-፰)

በሰኞ ዕለት ጌታችን ቤተ መቅደሱን ከነጋዴዎች ማጽዳቱና የሃይማኖቱን ሥርዓት ወደ ንግድ የለወጡትን ማስወጣቱ (ሉቃ. ፲፱፥፵፭) በቤተ መቅደሱ ላይ የበላይነት አለን የሚሉት የካህናት አለቆችና ጸሐፍት በእነርሱ ዘንድ “የጥቅም መነካት” ፈጥሮባቸው ነበር።

በነጋታው በዕለተ ሠሉስ ጌታችን በቤተ መቅደስ እያስተማረና ወንጌልን እየሰበከ ሳለ፣ እነዚህ መሪዎች ከሽማግሌዎች ሆነው በመምጣት ድንገተኛ “የሥልጣን ጥያቄ” አቀረቡ።

“ወይቤልዎ፥ ንግረነ በመባሕተ መኑ ትገብር ዘንተ? ወመኑ አብሐከ ትግበር ከመዝ? ንገረን ይህንን በምን ሥልጣን ታደርጋለህ? ወይስ ይህን ሥልጣን የሰጠህ ማነው? አሉት” (ሉቃ. ፳፥፪)

ይህንንም ሲሉ የሥልጣኑን ምንጭ፣ “የማድረግ መብት” ወይም “ሕጋዊ ፈቃድ” ማለታቸው ነው። እነርሱ ጌታችንን የጠየቁት እንደ አምላክ ሳይሆን “እኛ ካልሾምንህ፣ እኛ ካልፈቀድንልህ ቤተ መቅደሱን የማጽዳት መብት ከየት አገኘህ?” የሚል ለአንድ ሰው የሚጠየቅ በዘመኑ ቋንቋ የቢሮክራሲ ጥያቄ ነው።

ክፋት ልባቸውን ስላሳወረው በዓይናቸው የሚመለከቷቸውን ተአምራት አይቶ ከማመን ይልቅ ከባለሥልጣን የፈቃድ ወረቀት ጠየቁት። ለስሕተታቸው እውነተኛ ማስረጃ ማቅረብ ስለማይችሉ ይህንን ስሕተታቸውን የገለጠባቸውን እውነት ከመቀበል ይልቅ መለኮታዊውን እውነት በሰዋዊ ሥርዓት ለመለካት ሞከሩ።

ዛሬም በሕይወታችን ውስጥ እውነትና ቅድስና ሲመጣ ቀድሞ የሚቃወመን የልባችን ክፋት ጥቅመኝነት ነው። ሀገራችንንና ዓለማችንን ብሎም ቤተ ክርስቲያናችንን እየፈተነ ያለው ከእውነት መንገድ ይልቅ በሐሰት የተገነባ ዝና፣ ስግብግብነትና ሆዳምነት ነው።

በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በኑሯችን የአንድን ሰው መንፈሳዊ ፍሬ ከመመልከት ይልቅ፣ “ከየት መጣ? ማን ፈቀደለት? የእኛ ወገን ነውን? በሚል ሥጋዊ ቅናት የእግዚአብሔርን ሥራ እንቃወማለን።

ጸሐፍት ይህ መንፈሳዊ ውድቀታቸው ሳያንስ እውነትን ለመሸፈን ያደረጉት ጥረት ይደንቃል። ይህ ጥያቄያቸው በተንኮል የተሞላና በሁለት አማራጮች መካከል አጣብቂኝ ውስጥ የሚከት ጥያቄ ነበር።

➜ ሥልጣኔ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው ቢል፦ አንተ ራስህን አምላክ አድርገሀል ብለው ሊከስሱት ነው።

➜ ሥልጣኔ ከሰው ዘንድ ነው ቢል፦ “እንግዲህ ተራ ሰው ከሆንክ እንዲህ ያለውን ታላቅ ድርጊት የማድረግ መብት የለህም” ብለው በሕዝብ ፊት ሊከሱትና ሊያስሩት ዐቅደው ነበር።

ጌታችን ግን የእነርሱን ተንኮል ተረድቶ መልሱን በጥያቄ መለሰላቸው።

➜ “ጥምቀቱ ለዮሐንስ እምአይቴኑ ይእቲ እምሰማይኒ ወሚመ እምሰብእኑ፣ የዮሐንስ ጥምቀት ከሰማይ ነበረችን ወይስ ከሰው? አላቸው።” (ሉቃ. ፳፥፬)

ይህ የጌታ ጥያቄ ጠያቂዎችን በራሳቸው ጥያቄ ወጥመድ ውስጥ የሚከት ጥያቄ ነበር። ጌታ እነርሱ ሊያጠምዱበት ከዘረጉት ወጥመድ አልፎ እነርሱን በጥያቄ አጠመዳቸው። እነርሱ ባሰቡበት መንገድ አለመመለሱ ብቻ ሳይሆን እነርሱን አጣብቂኝ ውስጥ የሚከታቸው የመልስ ጥያቄ ሆነባቸው። ስለ እርሱ ማንነት በራሳቸው አንደበት እንዲመልሱ የሚያደርግ ጥያቄ ነበር።

ጌታችን ዮሐንስ መጥምቅን ጠቅሶ የጠየቃቸው ለምንድነው? ቢሉ

➜ ዮሐንስ መጥምቅ ስለ ክርስቶስ “እነሆ የእግዚአብሔር በግ” (ዮሐ.፩፥፳፱) ብሎ መስክሯልና ነው።

ስለዚህ እነርሱም “ከሰማይ ናት” ካልን፦ የዮሐንስን ምስክርነት መቀበልና በክርስቶስ ማመን ነበረባቸሁ ሊለን ነው። “ከሰው ናት” ካልን ደግሞ ሕዝቡ ዮሐንስን እንደነቢይ ስለሚያከብሩት ሕዝቡን በመፍራት በሁለት የአጣብቂኝ መልስ ውስጥ ገቡ።(ሉቃ. ፳፥፭-፮)

እግዚአብሔርን ብዙ ጊዜ “ለምን እንዲህ ሆነብኝ?” ብለን ስንጠይቅ፣ እርሱ ደግሞ “ቀድሞ የሰጠሁህን ጸጋ ምን አደረግከው?” ይለናል። (ማቴ.፳፭፥፲፭)

ጌታ እዚህ ጋር እያሳየን ያለው እውነትን ፍለጋ ወደ ውጭ ከመሄዳችን በፊት ወደ ውስጣችን እንድንመለከት ነው። ብዙ ጊዜ መልሱ እጃችን ላይ እያለ እኛ ግን እግዚአብሔርን “ሥልጣንህን አሳይ” እንለዋለን።

➜ በልባቸው ላይ ሐሰትን ያነገሡና እውነትን መቀበል የተሳናቸው ጸሐፍት ለጌታ ጥያቄ በቀጥታ ከመመለስ ይልቅ እውነቱን እያወቁ እንዳላወቁ ሆነው “መልሰውም፦ ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም አሉት።” (ሉቃ. ፳፥፯)

➜ “አናውቅም” የሚለው መልሳቸው በታሪክ ውስጥ እጅግ አሳፋሪ ውሸት ነው። እውነቱን ስለማያውቁ ሳይሆን ማወቅ ስለማይፈልጉ ነውና። “ከሰማይ ብንል….ከሰው ብንል….” እያሉ የሚያሰሉት ስለ እውነት ሳይሆን ስለ ጥቅማቸውና ስለ ደኅንነታቸው ነበር።

ዛሬም በዘመናችን “አናውቅም” ባዮች በዝተዋል። በሀገራችን፣ በቤ/ክ አገልግሎታችንና አጠቃላይ በማኅበራዊ ሕይወታችን እውነት ሲገለጥና ግፍ ሲሠራ እያየን፣ ጥቅማችን እንዳይነካ “አላየሁም፣ አልሰማሁም፣ አናውቅም” እንላለን።  “ብርሃን ወደ ዓለም መጣ፣ ሰዎች ግን ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ወደዱ” እንዲል ቅዱስ ዮሐንስ። (ዮሐ. ፫፥፲፱)

➜ “ኢየሱስም፦ እኔም በምን ሥልጣን እነዚህን እንዳደርግ አልነግራችሁም አላቸው።” (ሉቃ. ፳፥፰)

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህንን የጌታ መልስ ሲተረጉም ጌታ መልስ የከለከላቸው ሊቀበሉት ዝግጁ ስላልሆኑና ለእሪያ ዕንቁ ስለማይጣል መሆኑን ይናገራል። (ማቴ. ፯፥፮)

ሰው በልቡ ክፋትን፣ ቂምንና ተንኮልን ሸምቆ የሚጸልየው ጸሎት መልሱ ዝምታ ነው። “በልቤስ በደልን አይቼ ብሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር።” (መዝሙር ፷፯፥፲፰) በማለት ነቢዩ ዳዊት እንደተናገረ፡፡

ስለዚህ እኛም፡-

➜የእግዚአብሔርን ሥራ በራሳችን አእምሮ አንመዝን። “ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና” (፩ኛ ቆሮ.፩፥፳፭)

➜ ለእውነት ታማኝ እንሁን። እንደ ጸሐፍት በሰዎች ዘንድ የሚመጣብንን “ውግረት፣ ይሉኝታን፣ መገፋትና ሞትን ወዘተ ፈርተን እውነትን መካድ አይገባንም። እንደ ዳዊት “እስመ ለልየ አአምር ጌጋይየ ወኃጢአትየኒ ቅድሜየ ውእቱ በኵሉ ጊዜ፤ እኔ መተላለፌን (በደሌን) አውቃለሁና፥ ኃጢአቴም ሁልጊዜ በፊቴ ነውና።” (መዝ.፶፩፥፫) ብለን እውነት ሐሰትን እንዲያሸንፍ በፊቱ ለንስሐ መቅረብና ማልቀስ አለብን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር፤ ወለወላዲቱ ድንግል፤ ወለመስቀሉ ክቡር

የጥያቄ ቀን

ከኄራኒ ጠና

ጥያቄ ቀን

 ለፍጥረተ ዓለም ሶስተኛ ቀን የሆነችው ማክሰኞ በህማማት ሳምንት የጥያቄ/ የትምህርት ቀን ተሰኝታ፤ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀድሞ በተናገረውና ባደረገው ላይ አይሁድ ጥያቄ ማቅረባቸው እንዲሁም እርሱ መልስ በመስጠት ማስተማሩ ይዘከርባታል።

  • ጥያቄ

 ዕለቱን የጥያቄ ቀን ያሰኘው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ሰኑይ ያደረገውን አንጽሆተ ቤተ መቅደስ ተከትሎ ጸሐፍትና ፈሪሳውያን ይህንን ገበያ መፍታት፤ ተአምራትን ማድረግ ፤ ከምድራውያን ነገስታት ከሌዋውያን ካህናት ያይደለ ትምህርት ማስተማርን በምን ስልጣን ታደርገለህ? ይህንንስ ስልጣን ማን ሰጠህ? ሲሉ መጠየቃቸው ነው። (ማቴ ፳፩፥ ፳፫ – ፳፯)

ጸሐፍት እና ፈሪሳውያን ክርስቶስ ይህንን በማን ስልጣን አንደሚያደርግ ጠፍቷቸው አልነበረም ለጥያቄ የመጡት፤ ይልቁንም እርሱን ለመፈታተን እና ከቃሉም ስሕተትን ለማግኘት ነበር። ልቡና እና ኩላሊትን የሚመረምር ሁሉን አዋቂ አምላክ ግን የልባቸውን ጠማማ መሻት ቀድሞው አውቆ ነበርና ጥያቄያቸውን በሌላ ጥያቄ መለሰላቸው።

“ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ ደግሞ አንዲት ነገር እጠይቃችኋለሁ እናንተም ያችን ብትነግሩኝ እኔ ደግሞ እነዚህን በምን ሥልጣን እንዳደርግ እነግራችኋለሁ የዮሐንስ ጥምቀት ከወዴት ነበረች ከሰማይን ወይስ ከሰው አላቸው። እነርሱም እርስ በርሳቸው ሲነጋገሩ፦ ከሰማይ ብንል፦ እንኪያስ ስለ ምን አላመናችሁበትም ይለናል ከሰው ግን ብንል ዮሐንስን ሁሉም እንደ ነቢይ ያዩታልና ሕዝቡን እንፈራለን አሉ። ለኢየሱስም መልሰው፦ አናውቅም አሉት። እርሱም ደግሞ፦ እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንዳደርግ አልነግራችኹም አላቸው።” 

እነርሱ በሰው ዘንድ መከበሩን የቃሉ ትምህርትን መወደዱን አይተው ለማወቅ በቅንነት በመጠየቅ ፋንታ በቅናት ምን ብንለው እናሳጣዋለን ወጥመዳችን ውስጥ እናስገባዋለን ብለው አውጥተው አውርደው ጥያቄዎቻቸውን ይዘው መጡ ስለዚህም እንደ አመጣጣቸው መለሰላቸው።

እኛስ ዛሬ ምን ዓይነት ጥያቄ ይዘን ነው ወደ አምላካችን ብሎም ወደመምህራኖቻችን የምንቀርበው? በልባችን ክፉ ምኞትን ይዘን በንግግራችን ዋሽተንበት እንዳይሆን እንጠንቀቅ (ገላ ፮፥፯) በንፁሕ እና በተሰበረ ልብ ነው አምላካችን ፊት መቅረብ ያለብን እንጂ እንደ ጸሐፍት እና እንደ ፈሪሳውያን ነገር ጐንጕነን ሊሆን አይገባም፤ ስንጠይቅ አውቀን ለመራቀቅም አይሁን ይልቁንም በሕይወት ለመኖር እንጠይቅ፤ አዋቂ ነው/ናት ለመባል ለትዕቢትም አይሁን/ ለመረዳት እንጂ፤ የሰውን ስህተት ለማጕላትና ለመሰናክል አይሁን፤ እንዳጠቃላይ ከእርሿቸው መጠበቅ እንዳለብን አምላክ ነግሮናልና ልጠነቀቅ ይገባናል።

  •  ምሳሌዎች

 ክርስቶስ ጥያቄያቸውን በዚህ መንገድ ካስተናገደ በኋላ በምሳሌ ያስተምራቸው ጀመር ሁለት ምሳሌዎችንም ነገራቸው።

 ምሳሌ አንድ: – ፪ ልጆች የነበሩት አንድ ሰው ነበረ፤ ወደ አንደኛው ልጁም ሄዶ ልጄ ሆይ በወይን አትክልቴ ሥራ አለው፤ እርሱም ሊሠራ አልወደደም፤ ኋላ ተመልሶ ግን ተጸጸተ ሠራም፤ አባትየው ወደ ሌላኛው ልጁ አቀና እንዲህም አለው፤ ሌላኛውም ልጅ እሺ አለ አልሰራም ከሁለቱ የአባቱን ፈቃድ የፈጸመው ማን ነው? አላቸው። እነርሱም የፊተኛው አሉት።

 በዚህ ምሳሌ አባት የተሰኘው እግዚአብሔር ሲሆን፤ የመጀመሪያው ልጅ ደግሞ በንስሐ የተመለሱ ቀራጮችን ይወክላል፤ ሁለተኛው ልጅ ደግሞ ጸሐፍትና ፈሪሳውያንን ይወክላል። ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ይህንን ሲያብራራ እግዚአብሔር ከንግግራችን ይልቅ ሥራችንን እንደሚፈልግ ይነግረናል፤ ንግግራቸውን ካቀኑ መልካሙን ቃል ከሚናገሩ ነገር ግን በግብራቸው ከሚበድሉ፤ ክርስቶስም ራሱ “ስለዚህ ያዘዟችሁን ሁሉ አድርጉ ጠብቁትም ነገር ግን እየተናገሩ አያደርጉትምና እንደ ሥራቸው አታድርጉ” (ማቴ ፳፫፥፫) ካላቸው ጸሐፍትና ፈሪሳውያን ቀድመው በቀደመ ሕይወታቸው ያላመኑ እንዲሁም የበደሉ ነገር ግን በንስሐ የተመለሱ ቀራጮች መንግሥቱን ይወርሳሉ አለ። እኛ አሁንም ከዚህ ምሳሌ እኒህን እንማራለን: –

  1.  የአንደበት ብቻ ሳይሆን የተግባርም ክርስቲያን ልንሆን እንደሚገባ

ውጫዊ በሆነው ሰው በሚያየው በመድረክና በማህበራዊ ሚዲያ ስለ እምነታችን መመስከር ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር በሚያየው ሰው በማያየው የግል ሕይወታችንም መልካሙን ምግባር ልንሠራ ይገባናል። ይህም ያለንን እውቀት፣ ገንዘብ የመሳሰሉትን ለተቸገሩ በመመጽወት ፤ በፍጹም ትሕትና እና ፍቅር ከሁሉ ጋር በመኖር…. ሊገለጽ ይችላል።

  •  አሁን አንዳልረፈደ

ልክ እንደቀራጮች ለእግዚአብሔር እምቢ ያልንባቸው ከሕጉም ያፈነገጥንባቸው ጊዜያት ቢኖሩም የምሕረት አባት የሆነው አምላካችን በንስሐ ሊቀበልን ከመንጋውም ሊቀላቅለን የታመነ ነውና፤ ኑ ዛሬ ነገ ሳንል በንስሐ ወደ አምላካችን እንመለስ።

 ምሳሌ 2: –

‹‹ባለቤት ሰው ወይንን ተከለ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፤ መጭመቂያም አስቈፈረለት፤ ግንብም ሠራለት፤ ለገባሮችም ሰጥቶአቸው ሄደ፡፡ የሚያፈራበት ወራት በደረሰ ጊዜም፥ ከወይኑ ፍሬ ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮችን ወደ ገባሮቹ ላከ፡፡ ገባሮቹም አገልጋዮቹን ይዘው፥ አንዱን በበትር ደበደቡት፤ አንዱንም ገደሉት፤ ሌላውንም በድንጋይ መቱት፡፡ ከዚያም በኋላ ከቀደሙት የሚበዙ ሌሎች አገልጋዮችን ላከ፤ እነርሱንም እንዲሁ አደረጉባቸው፡፡ በኋላም ልጄንስ ይፈሩት ይሆናል ብሎ ልጁን ላከ፡፡ ገባሮቹም ልጁን ባዩት ጊዜ እርስ በርሳቸው፡- እነሆ፥ ወራሹ ይህ ነው፤ ኑ እንግደለውና ርስቱን እንውረስ ተባባሉ፡፡ ይዘውም ከወይኑ ቦታ ወደ ውጭ አውጥተው ገደሉት፡፡›› (ማቴ ፳፩ ፥፴፫-፴፱)

በዚህም የምሳሌ ትምህርት የመሬቱ ባለቤት እግዚአብሔር አብ ሲሆን፤ ግንብ፣ ቅጥር እና መጭመቂያ የተሰኙት ደግሞ መቅደሱ፣ የኦሪት ሕግና መሰዊያው ነበሩ፤ ገበሬዎች ደግሞ የአይሁድ ካህናትና አባቶች ናቸው፤ ሰራተኞቹ የተባሉት በየዘመናቱ የተላኩ ነብያት ሲሆኑ፤ የተወደደው ልጅም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።

ጌታችን በዚህ ምሳሌ የተናገረው በአጭሩ ከብሉይ ወደ ሐዲስ ኪዳን የተደረገውን ሽግግር ነው። እግዚአብሔር የወይን አትክልት ስፍራ ለተባለችው ለእስራኤል እና ለተመረጠው ሕዝቧ በየዘመኑ ነብያትን ልኮ እንዳስተማራቸው፤ እነርሱም በነብያቱ መከራን እንዳጸኑባቸውና እንደገደሏቸው ይህንንም እየተመለከተ ስለ ምሕረቱ ብዛት በድጋሚ ነብያቱን እንደላከ መልሰውም ያንኑ እንዳደረጉባቸው ከዚያም በመጨረሻው የሚወደውን አንዱን ልጁ የተባለው ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደላከ በእርሱም እንዳላመኑበት ይልቁንም  በእንጨት መስቀል እንደሰቀሉት ያሳየናል።

ይህም በውጤቱ የወይኑ ስፍራ በክርስቶስ ካላመኑት አይሁዳውያን ተወስዶ ለአዲሶቹ ገበሬዎች በክርስቶስ ላመኑት ለአሕዛብ መሰጠቱን እና ሐዋርያዊ የሆነች ቤተክርስቲያን መመሥረቷን ያሳየናል።

 ከዚህም ምሳሌ እኛ የሚከተሉትን ልንማር ይገባናል: –

  1.  በቤተ ክርስቲያን ያለን ስልጣን ለብቻው ለድኅነታችን ዋስትና እንደማይሆን፤

በምሳሌው ገበሬ የተሰኙት የአይሁድ መንፈሳዊ መሪዎች ካህናት የነበራቸው ስልጣን አላዳናቸውም፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር ከእነርሱ የጠበቀውን መልካሙን የምግባር ፍሬ አላፈሩምና። አሁንም እኛ ምንም እንኳ በመድረክ ብንዘምር ስነ-መለኮት አዋቂ ነን ብንል መልካሙን ፍሬ ትሕትናን፣ ፍቅርን ፣ መታዘዝን ገንዘብ ካላደረግን እኒህ ለእኛ ምንም ጥቅም እንደማይሰጡን ነው።

  •  ክርስቶስን መካድ የክሕደት ሁሉ መጨረሻው እንደሆነ

 አይሁድ ልጁ ወራሹ መጣ እርሱን ብንገድል ውርሱን እንወስዳለን ብለው እንዳሉትም አደረጉ፤ ያን ጊዜም ሁሉን ነገር አጡ። እኛም ዛሬ በስሕተት ትምህርት ተወስደን ክርስቶስን እንደ አምላክነቱ ባንቀበለው እንደ አይሁድ ሁሉን እናጣለን። በአገልግሎታችንም ሆነ ከሁሉም ነገር በፊት የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት እና ጌትነቱን በፍጹም ልብ ልናምን ይገባናል። የሐዲስ ኪዳኗ ሐዋርያዊት ቤተክርስቲያንም በዚህ እውነት ላይ ተመስረታለችና። (ማቴ ፲፮ ፥ ፲፰)

  •  የአሁኑ ገበሬዎች እኛ ነን!

 የወይን ቦታው አሁን ለሌላ ፍሬውን ለሚያፈሩ ገበሬዎች ተሰጥቷል፤ ሌሎቹ ገበሬ የተሰኘችው የሐዲሷ ቤተ ክርስቲያን ኅብረት ናት፤ ያህ ማለት እኔ፣ አንተ፣ አንቺ ሁላችንም የቤተክርስቲያን አባላት ማለት ነን። ታዲያ እኛ እውነት ፍሬ እያፈራን ነውን? እኛ የወይን ፍሬው ባለ አደራዎች እንጂ ባለቤቶች አይደለም፤ እናም ባለቤቱ መጥቶ በሰጠኋችሁ ሃይማኖት ሕግ እና ሥርዓት ምን መልካም ፍሬ አፈራችሁ? ቢለን የምንመልሰው አዘጋጀተናልን? ለዚህም ነው በየቀኑ ራሳችንን ለእግዚአብሔር መንግሥት የሚሆን ምን ፍሬን እያፈራን እንደሆነ ልንጠይቅና በማስተዋልም ልንኖር የሚገባል።

  •  ትምህርት

 በዕለተ ሠሉስ ከላይ ከተነጋገርነው ከጸሐፍት፣ ከፈሪሳውያን እና የጌታችን መልስ ባሻገር ክርስቶስ በቤተ መቅደስ ያስተማረው ረጅም ትምህርትም ታስቦ ይውላል። (ሉቃ ፳፩፥፪-፴፮)

በዚህም ጌታችን በመጀመሪያ የመበለቲቱ ሁለት ሳንቲም መባእ አመስግኗል፤ በዚያ ብዙ ወርቅ እና ሌላ ውድ የሆነ መባን የሚያገቡ ብዙዎች እያሉ ለምን የእርሷን ሁለት ሳንቲም መባእ አመሰገነ? ቢሉ ሌሎቹ ትርፍና ኪሳራቸውን አስልተው ሲሰጡ እርሷ ግን ያላትን ያለስስት ሰጥታለችና። የአቤልን መሥዋዕት የወደደ ያው እግዚአብሔር አሁንም ከስጦታው ብዛት ይልቅ የልቧን ንጽሕናና ከጎዶሎዋ ላይ ሳትሰስት መስጠቷን አደነቀ።

ጌታችን ዛሬም ቢሆን ያንኑ ስጦታ ይወዳል፤ ያለን ሁሉ ከእርሱ ነውና ለእርሱ ክብር ልናውለውም ይገባል አምላካችን እኮ አይደለም ብርና ንብረት ሕይወትም የሚሰጠው ነው ይህንንም እንኳ ብናደርግ እርሱ ካደረገልን ጥቂቱን እንኳን አንመልስም።

ከዚህም በተጨማሪ በዚህች እለት አምላካችን ስለ ዳግም ምጽአቱ እና ከእርሱ በፊት ስለሚፈጠሩት ነገሮች ከቤተ መቅደሱ መፍረስ ጋር አያይዞ በሰፊው አስተምሯል። ይህንንም ብቻ ተናግሮ ዝም አላለም፤ ምን ልናደርግ እንደሚገባንም ‹‹ራሳችሁን ጠብቁ፤ በመብልና በመጠጥ፥ በመቀማጠልና የዓለምን ኑሮ በማሰብ ልባችሁን አታደንድኑ፤ ያቺ ቀንም በድንገት ትደርስባችኋለች፡፡ በምድር በሚኖሩት ሁሉ ላይ እንደተዘረጋች ወጥመድ ትደርሳለችና፡፡ እንግዲህ ከዚህ ከሚመጣው ሁሉ በጸሎታችሁ ማምለጥ እንድትችሉ፥ በሰው ልጅ ፊትም እንድትቆሙ ሁልጊዜ ትጉ፡፡›› (ሉቃ ፳፩፥፴፬-፴፮) ሲል ነግሮናል። እኛም በዳግም ምጽዓቱ የምናምን ይህንን በማሰብ ማስታዋል እንኑር!

በአጠቃላይ በዚች የሰሙነ ሕማማት ማክሰኞ የአይሁድን ጥያቄ እና የጌታችንን ትምህርት አስበን እንውላለን። ከሁሉ በላይ በዕለቱ የሚነገረውን የእግዚአብሔር ቃል እንደ ሕይወታችን ስንቅ ልንወስደው ይገባናል። ካስተማሩት ብዙ እንደሚጠብቁበት ጌታችንም በአንድም በሌላ ካስተማረን ከኛ ፴(ሠላሳ)፣ ፷(ስልሣ) እና ፻(መቶ) ያማረ ፍሬን ይጠብቃልና የተማርነውን በኑሮ እናትርፍበት! ልክ በቅዳሴ እንደምንታዘዘው ‘አልዕሉ አልባቢክሙ/ልቡናችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ’ ተብለን በምድር ብንኖርም ልቡናችንን ወደላይ ወደ ሰማይ ከፍ አድርገን ከምድራዊ ፍላጎት በላይ በሆነው በእግዚአብሔር ሐሳብ ሕይወታችንን እንምራ።

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ ወለወላዲቱ ድንግል፤ ወለመስቀሉ ክቡር ለዓለም ዓለም አሜን።

መርገመ በለስ

ከመምህር አበበ ፍቅሬ

̎ስንዱ እመቤት” የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሀገራችን ኢትዮጵያ ሀገራዊ የዘመን አቆጣጠር፤ (calendar) ሰርታ ያስረከበች እንደመሆኗ መጠን የእያንዳንዱ የነገረ መለኮት አስተምህሮ፣ ሥርዓተ አምልኮ፤ (Liturgical worship) ፣ አጽዋማት፤ (fasts) ፤ ክብረ በዓላት እኒህን የመሳሰሉ ሁሉ የምታከናውነው ከታላቁ መጸሐፍ ቅዱስ መሠረት አድርጋ በዘመን ቀመር ነው። (ዘፍ. ፩፥፲፬)

ዓመት፣ ወር፣ ሳምንት፣ ቀን፣ ሰዓት እያለ እስከ ሣድሲት መለኪያ በዘመን መስፈሪያ ውስጥ አካታ ቀመራትን ከጥንታት እንደ ̎ድርና ማግ” አሰናኝታ ወቅቶችን በሚገባ አሰናድታ ስትዋጅ እነሆ ሦስት ዐሥር ምእት ዓመታትን ዘልቃለች።

ኢትዮጵያዊው የዜማ ደራሲ ቅዱስ ያሬድ ዐቢይ ጾምን ከአስተምህሮ አንጻር በስምነት ሣመንታት መክፈሉ እሙን ነው። የቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት ሥግው ቃል ክርስቶስ ሰው ከመሆኑ በፊት የነበረብንን የሞት ጥላ እንዲሁም የጌታችንን መከራ መስቀል አመጸኛው አዳምን ነፃ ለማውጣት እንደ አመጸኛ ተቆጥሮ የደረሰብን ስቃይ ሁሉ በዓይነ ኅሊናችን ስለን በመከራው ተባብረን በትንሣኤው አንድ እንድንሆን (ሮሜ ፮፥፭) በሚል የዐቢይ ጾም ሳምንታት የመጨረሻዎቹ አምስቱ ቀናት ሰሙነ ሕማማት በሚል ጠርቷቸዋል። የእያንዳንዱ እለታት ከአስተምህሮ ጋር በተያያዘ የራሳቸው ስያሜ ያላቸው ሲሆን፤ የመጀመሪያው የሕማማት እለት ሰኞ ̎መርገመ በለስ፤ የበለስ መረገም” በሚል ተጠርቷል።

ስለበለስ መረገም

̎በማለዳም ወደ ከተማ ሲመለስ ተራበ። በመንገድም አጠገብ በለስ አይቶ ወደ እርስዋ መጣ፤ ከቅጠልም ብቻ በቀር ምንም አላገኘባትምና፦ ለዘላለሙ ፍሬ አይገኝብሽ አላት፤ በለሲቱም ያንጊዜውን ደረቀች።” (ማቴ. ፳፩፥፲፰-፲፱) እንደሚለን ቅዱስ ማቴዎስ አምላካችን በሕጻናቱ አንደበት እንደተመሰገነ ወደቢታንያ አቀንቶ ሰለነበረ ከቢታንያ ሲመለስ ተርቦ ወደበለስ እንደሄደ፣ ፍሬ እንዳላገኘና እንደረገማት ነው የሚያስረዳን።

የአንድምታ ሊቃውንት በትርጓሜ ወንጌል እንዳስቀመጡት በለስ ለሚለው የተለያዩ ትርጉም ሰጥተው ይበይኑታል፤ በዚህም መሠረት

በለስ ቤተ እስራኤል ነው፤ ̎ሕዝበ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ሕዝብ፣ አምላከ እስራኤል፤ የእስራኤል አምላክ” ተብሎ በስሙ የተጠሩት፣ በስማቸው የተሰየመው እንደውም ̎ወልድየ ዘበኲርየ፤ የበኲር ልጄ” ብሎ በቁልምጫ የሚጠራቸው፤ ̎መጽአ ኃበዚአሁ፤ የእርሱ ወደ ሆኑት ወደ ወገኖቹ መጣ።” (ዮሐ. ፩፥፲፩) ብሎ ዮሐንስ በወንጌሉ እንደ ነገረን ወዳጆቹ ተብለው የሚጠሩት ናቸው።

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን በጠላት እጅ ቢወድቁ በዐሥር ታላላቅ ተአምራት ያስለቀቃቸው፣ ፈርዖን እግር ለእግር ቢከታተላቸው በባሕር ያሰጠመላቸው፤ ከአለት ውሀ አፍልቆ ያጠጣቸው፤ ከሰማይ መና አውርዶ የመገባቸው፤ ወደ ከነአን መርቶ ያወጣቸው፤ አሕዛብን አስለቅቆ ከነአንን በመሐላው መሰረት ያወረሳቸው፤ ሲያምጹ እንደልጅ አማሌቃውያንን አስነስቶ የቀጣቸው መልሰው ሲያለቅሱ ደግሞ በወዳጆቹ የታደጋቸው፤ አምላክ ሰው ሆኖ በመካከላቸው ተገልጦ “እውነት እላችኋለሁ፥ ብዙዎች ነቢያትና ጻድቃን የምታዩትን ሊያዩ ተመኝተው አላዩም፥ የምትሰሙትንም ሊሰሙ ተመኝተው አልሰሙም።” (ማቴ. ፲፫፥፲፯) ፤ ̎አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው።” (ዮሐ. ፰፥፶፮) እያለ ቢነግራቸውም ̎ገና አምሳ ዓመት ያልሆነህ አብርሃምን አይተሃልን? አሉት ̎ (ዮሐ. ፰፥፶፯) እንዲያውም “ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ።” (ዮሐ. ፰፥፶፱) እንዲል በሥጋ መገለጡን ሲያዩ ሰውነቱን እንጂ መለከታዊ አካሉን ማየት አልቻሉም፤ ብሉየ መዋእል ጌታን በዕድሜ ገድበውታል። ̎…እነርሱ ግን አልተቀበሉትም።” ዮሐ. ፩፥፲፩) እንዲል ካዱት።

“አብርሃም አባት አለን እንደምትሉ አይምሰላችሁ፤” (ማቴ. ፫፥፱) “መልሰውም፦ አባታችንስ አብርሃም ነው አሉት። ኢየሱስም፦ የአብሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር።” (ዮሐ. ፰፥፴፱) እንዲል ቤተ እስራኤል ስም ብቻ ይዘው የቀሩ ምግባር የጎደላቸው በኢየሱስ ክርስቶስ ከማመን የዘገዩ ነበሩ።

ጌታችን ፍሬ ምግባርና ሀይማኖትን ፈልጎ በመጣ ጊዜ ቅጠል የአብረሀም ዘር መባልን ብቻ ሆነው ቀሩ። በመሆኑም ̎ለዘለዓለም ፍሬ አይገኝብሽ።” ብሎ ረገማት፤ በዚሁ ቃል መሠረት ምንም እንኳ እንደነ ቅዱስ ጳውሎስና እሱን የመሰሉ የወንጌል አርበኞች ቢገኙም ቤተ እስራኤል የብሉይ አማኝ ብቻ ሆና በመቅረት በክርስቶስ ኢየሱስ የሆነው የሐዲስ ኪዳን ሕግን ከመቀበል ገሸሽ ብላለች። እስካሁን የጌታ መምጣቱን ሳትቀበል ገና እንደሚመጣ ስትጠባበቅ በዘመናችን ትገኛለችና፤ ቤተ እስራኤል የሚጠበቅባትን የሀይማኖትና የምግባር ፍሬ ሳይገኝባት በመቅረቷ ተረገመች ወዲያው ደረቀች።

በለስ የተባለች ኦሪት ናት። መተርጕማኑ እንደሚተረጉሙት ኦሪት ̎ፈጻሜ ሕግ፤ የሕግ መፈጸሚያ ከመባል ውጭ ድኅነትን አላደረገባትም። ማለትም ይህንን አድርጉ ይህንን አታድርጉ ብቻ ትእዛዝን ነበር፤ መጽሐፍ ቅዱስ ̎እንኪያስ ሙሴ የፍችዋን ጽሕፈት ሰጥተው እንዲፈቱአት ስለ ምን አዘዘ? አሉት። ሙሴስ ስለ ልባችሁ ጥንካሬ ሚስቶቻችሁን ትፈቱ ዘንድ ፈቀደላችሁ፤ ከጥንት ግን እንዲህ አልነበረም። (ማቴ. ፲፱፥፯-፰) እንደሚለው ሕግን ለመፈጸም የተሰጡ አሉና፤ እንዲሁም መሥዋዕትና ሥርዓተ ክህነቱ ጊዜያዊ ድኅነትን ያሰጡ ዘንድ ፍጹም ድኅነትን ማሰጠት የማይችሉ ሕግጋት ነበሩ። ስለዘህም ሻራቸው፤ ̎እምከመ ተሥዕረት መሥዋዕቶሙ ትሠዐር ክህነቶሙ፤ መሥዋዕታቸው ከተሻረች ክህነታችውም ትሻራለች እንዲል መሥዋዕቱ ከነሙሉ የመሠዊያ ሥርዓቱ ተሻረ፤ ምክንያቱም ዘለዓለማዊ የሆነ የነፍስ ድኅነት በሚያሰጠው በአማናዊ መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ተቀይሯልና ነው።

የክህነት አሰጣጡም ቢሆን ተቀይሯል፤ ቀደም ሲል ክህነት ከሌዊ ወገን ከሆነው ከአሮን ቤት ብቻ ነበር፤ በክህነቱም የሚሠዋው ደመ ነፍስ እንስሳ ሆኖ የሚፈውሰውም ሥጋን ብቻ ነበር፤ የሚታየውም ነቀፋ ነውረ ሥጋ ነበር፤ የሐዲስ ኪዳን ክህነት ግን ሕዝብና አሕዛብ ብሎ በነገድ(ወገን) ሳይለይ በክርቶስ ያመነ ሁሉ የሚሰጥ ክህነቱም የዘለዓለም ኃጢአት ማስተስሪያ ነው፤ መስፈርቱም ነውረ ሥጋ ሳይሆን ነውረ ነፍስ የሆነው ኃጢአት ነው።

ከዚህም ባሻገር ̎ዓይን ቤዛ ዓይን/ ዓይን ያጠፋ ዓይኑ የጥፋ” ተብለው የተሰጡት ዓየነት ሕጎችን “…ከእናንተ ኃጢአት የሌለበት አስቀድሞ በድንጋይ ይውገራት አላቸው።” (ዮሐ. ፰፥፯) “እኔም አልፈርድብሽም፤ ሂጂ ከአሁንም ጀምሮ ደግመሽ ኃጢአት አትሥሪ አላት።” (ዮሐ. ፰፥፲፩) ማንም ስለኃጢአቱ ንሰሐ እንዲገባ እንጂ እንዳይገደል አምላካችን አዟል።

በለስ የተባለው ኃጢአትን ነው። መተርጕማኑ ̎የበለስ ቅጠል ሰፊ እንደሆነ ኀጢአትም በዚህ ዓለም ሰፍና አገኛት።”፤ አንድም በለስ ሲበሉት ይጣፍጣል ቆይቶ ይኮመጥጣል። ኃጢአትም ሲሠሩት ደስ ያሰኛል ኋላ ያሳዝናልና…ፍሬ አይገኝብሽ አላት በአንቺ በመጣ ፍዳ የሚያዝ አይኑር አላት። ኃጢአትም ፈጠና ጠፋች።”

በቀዳማዊ አዳም ምክንያት ሁላችንም ተላላፊዎች ተብለን በኃጢአት ባርነት ሥር ብንሆንም በዳግማዊ አዳም በኢየሱስ ክርስቶስ የተነሳ ሁላችንም ከበደል ከፍደ ነፃ ወጣን፤ በዚህም ማንም በአዳም መተላለፍ የሚጠየቅ እንደሌለና፤ ሁሉም ራሱ ወዶ ፈቅዶ በሚሠራት ኃጢአት የሚጠየቅ መሆኑን አስረዳን።

በባሕርዩ በደል የማይስማማው ንፁሐ ባሕርይ ክርስቶስ ሳይበድል በደለኛ ተብሏል፤ ከወንበዴዎች ጋራ ተሰቅሏል። በእንዲህ ዓይነት ሁኔታ ከባርነት ቀንበርም አላቆናል። መተርጕማኑ እንዳስቀመጡትም ̎ኃጢአት ከሥሩ እንደተነቀለ ዛፍ ሆኗል፤ ከዚህ በኋላ ኃጢአት የሚሰራ ሰው ለተማረከ ወታደር የሚያገለግል ሰው ይመስላል።” 

 ዛሬም አምላካችን ከእያንዳንዳችን ፍሬ ሊፈልግ ይመጣል፤ ገበሬ የተከለው ችግኝ ኮትኵቶ፣ ውሀ አጠጥቶና አርሞ ካሳደገው በኋላ የድካሙን ፍሬ ከዛፉ እንደሚጠብቅ ሁሉ እስከ ሞት ድረስ የሚያደርስ ውድ ዋጋ የከፈለልን አምላካችን ከሁላችንም ፴፣ ፷ና ፻ የሃይማኖት ፍሬ የፈልግብናል

ከዚህ ውጪ ግን ፍሬ የማይገኝብን ከሆነ ̎አሁንም በወይኔ ላይ የማደርገውን እነግራችኋለሁ፤ አጥሩን እነቅላለሁ፥ ለማሰማርያም ይሆናል፤ ቅጥሩንም አፈርሳለሁ፥ ለመራገጫም ይሆናል። ባድማ አደርገዋለሁ፤ አይቈረጥም፥ አይኰተኰትም፤ ኵርንችትና እሾህ ይበቅልበታል፤ ዝናብንም እንዳያዘንቡበት ዳመናዎችን አዝዛለሁ።” (ኢሳ. ፭፥፭-፮) አንዲል ለመከራና ለዋይታ ተላልፈን መሰጠት ይኖራልና፤ ይህ እንዳይሆንብን ከወዲሁ አምላክ በልግስናው በሰጠን ዕድሜያችን ቃሉን ሰምተን እርሱን ደስ የሚያሰኝ ሥራ ልንሰራ ይገባናል። ማለትም

የሀይማኖት፣ የምግባር፣ የፍቅር፣ የአንድነት፣ የመተሳሰብ፣ የመቻቻል ፍሬ ሊፈልግ ይመጣል፤ ለእኛ ብሎ የተቀበላቸውን ጸዋትወ መከራዎችን አስበን እነዚህን ፍሬ አፍርተን ልንጠብቀው ይገባል።

ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይቆየን

ሆሣዕና በአርያም!

ከመምህር ጌራ ሞገስ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ አሜን። በባሕርዩ ሞት በመንግሥቱ ሽረት የሌለበት፤ አንድነቱን ሦስትነቱ የማይከፋፍለው ሦስትነቱን አንድነቱ የማይጠቀልለው ለዘለዓለም አንድ ሲሆን ሦስት ሦስት ሲሆን አንድ እየተባለ የሚመሰገን እግዚአብሔር አምላክ ወዶና ፈቅዶ እንኳንም ለ ፳፻፲፰ ዓ.ም በዓለ ሆሣዕና በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ።

ሆሣዕና

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ከዘለዓለማዊ ሞት የማዳን ሥራውን ለመፈጸም ጥቂት ቀናት ሲቀሩት በነቢያት የተነገረው ትንቢትና በብሉይ ኪዳን የነበረው ምሳሌ ይፈጸም ዘንድ በአህያዪቱና በውርንጫው ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ደቀ መዛሙርቱና ብዛት ያለው ሕዝብ ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› እያሉ በመዘመር ሰማያዊ አዳኝ መሆኑን መስክረው ተቀብለውታል። ሆሣዕና ቃሉ የአረማይክ ሲሆን ትርጉሙም “አሁን አድን” ማለት ነው፡፡

የሆሣዕና በዓል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የትሕትና ንጉሥነት እና የድል ጉዞ የምናስብበት ታላቅ ዕለት ነው። ይህ በዓል በታሪክ ውስጥ የተከናወነ ድርጊት ብቻ ሳይሆን፣ ዛሬ ላለንበት ዘመንና ሕይወት ጥልቅ የሆነ መንፈሳዊ ትርጉም አለው።

ሆሣዕናን እና ያለንበትን ዘመን በሚከተሉት ዋና ዋና ነጥቦች ማየት እንችላለን፦

. ትሕትና እንደ መሪነት መገለጫ

በዓለ ሆሣዕና የዓለምን የሥልጣንና የክብር ትርጉም የለወጠ ዕለት ነው። በወቅቱ የነበሩ ነገሥታት በፈረስና በሰረገላ፣ በጦር መሣሪያ ታጅበው ለጦርነትና ለግርማ ሞገስ ሲወጡ፣ የሰላሙ ንጉሥ ግን በአህያ ውርንጭላ ላይ ሆኖ መጣ።

 “ለጽዮን ልጅ፦ እነሆ፥ ንጉሥሽ የዋህ ሆኖ በአህያ ላይና በአህያይቱ ግልገል በውርንጭላዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል በሏት ተብሎ በነቢይ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ይህ ሆነ።” እንዲል (ማቴ. ፳፩፥፬-፭) ፤ ዘካ. ፱-፱)

በዘመነ ብሉይ የነቢያቱ ትርኢት ትርጓሜ ወንጌል እንደሚነግረን ዘመኑ ሰላም ሲሆን ነቢይ ወደ ሕዝብ አደባባይ የሚሔደው በአህያ ላይ ተጭኖ ነበር፤ ዘመኑ እስራኤላውያንን እግዚአብሔር ተቆጥቷቸው የጦርነት በር የሚከፈትባቸው እንደሆነ ግን በፈረስ ላይ ተቀምጠው በግልቢያ ነበር የሚከሰቱት፤ የሰላም አለቃ የተባለው ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሥቃይ፣ የመከራ፣ የሰቀቀን ፣ የዋይታ በአጠቃላይ የዲያብሎስ ምርኮ የሆነበት የብሉይ ኪዳን ዘመን አከተመ፤ የሰላም፣ የዕረፍት፣ የሐሴትና የነፃነት ዘመን ተወጠነ ሲል በአህያ ላይ ተቀምጦ መጣ።

ለዘመናችን ትምህርት፦ በዚህ በትዕቢትና በፉክክር በተናወጠ ዓለም ውስጥ፣ እውነተኛ ታላቅነት የሚገኘው በትሕትናና ሌሎችን በማገልገል እንደሆነ ያስገነዝበናል።

. የልብን ምንጣፍ ማንጠፍ (እውነተኛ አምልኮ)

በዓለ ሆሣዕና ሕዝቡ ልብሳቸውንና የዘንባባ ዝንጣፊዎችን በመንገዱ ላይ አነጠፉ። ዛሬ ደግሞ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው የውጭ ልብስን ሳይሆን፣ የልባችንን መከፈትና ንስሓን ነው።

 “ከሕዝቡም እጅግ ብዙዎች ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ፥ ሌሎችም ከዛፍ ዝንጣፊዎችን እየቆረጡ በመንገድ ላይ ያነጥፉ ነበር።” (ማቴ. ፳፩፥፰)

ለዘመናችን ትምህርት፦ ጌታ ወደ ሕይወታችን እንዲገባ የልባችንን ዙፋን ልንሰጠው ይገባል። በይሉኝታና በዘልማድ ብቻ ሳይሆን፣ ውስጣዊ ማንነታችንን ለእርሱ ማስገዛት ይጠበቅብናል።

. “ሆሣዕና” – የድኅነት ጩኸት

“ሆሣዕና” ማለት “አሁን አድን” ማለት እንደመሆኑ፤ በወቅቱ የነበሩ ሕዝቦች ጌታን የተቀበሉት እንደ ፖለቲካ ነፃ አውጪ ቢሆንም፣ እርሱ ግን የመጣው ከኃጢአትና ከዘለዓለም ሞት ሊያድነን ነው።

 “የሚቀድሙትም ሕዝብ የሚከተሉትም፦ ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር።” (ማቴ. 21፡9)

ለዘመናችን ትምህርት፦ ዓለማችን በጦርነት፣ በበሽታና በጭንቀት በታወከችበት በዚህ ዘመን፣ የእኛም ጩኸት “ሆሣዕና – ጌታ ሆይ አሁን አድነን!” ሊሆን ይገባል። እውነተኛ ሰላም ከሰው ሳይሆን ከእግዚአብሔር ብቻ እንደሚገኝ ማመን አለብን።

. የማይለወጥ አቋም (ጽናት)

በሆሣዕና ዕለት “ሆሣዕና” ያሉ ብዙዎች፣ ይሁኑ እንጂ ከጥቂት ቀናት በኋላ ሆሣዕና ብለው ባመሰገኑበት አንደበት “ስቀለው!” በማለት ሲጮኹ ታይተዋል። ይህም የሰው ልጅን ጠባይና የዘመናችንን ክዳት ያሳያል።

ለዘመናችን ትምህርት፦ እምነታችን በሁኔታዎች ላይ የተመሠረተ መሆን የለበትም። ነገሮች ሲመቻቹ የምናመሰግን፣ ሲከፉ ደግሞ የምናማርር መሆን የለብንም። “እስከ መጨረሻው የሚጸና እርሱ ግን ይድናል።” (ማቴ. 24፥13)

ሲጠቃለል ሆሣዕና የሰላም ንጉሥ ወደ ልባችንና ወደ ቤታችን የሚገባበት በዓል ነው። ዛሬም ጌታ በደጃችን ቆሞ ያንኳኳል። እኛም እንደ ኢየሩሳሌም ሕዝብ በደስታ ተቀብለን፣ በሕይወታችን ላይ እንዲነግሥ በመፍቀድ፣ ክርስቶስን መስለን ልንኖር ይገባል።

ወስብሐት ለእግዘአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ይቆየን

መልካም የሆሣዕና በዓል!

አገልግሎት

በዲ/ን አብርሃም ባንቲሁን

የሰው ልጅ በፈጣሪው አምሳል ሕያው ባለአእምሮ፤ ነቢብ ሆኖ ሲፈጠር የእግዚአብሔርን ስም ይቀድስ ዘንድ እንዲሁም ዓለም ሳይፈጠር በፊት የተዘጋጀለትን ዘለዓለማዊ ክብር ይወርስ ዘንድ ነው። የእግዚአብሔርን ስም ከሚቀድስባቸው መንገዶች ውስጥ አንዱ ሥጋ እንደ  ለበሰ መልአክ ሆኖ ለአገልግሎት በመትጋት ነው። ‹‹እኛ ፍጥረቱ ነንና እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን በማለት ንዋየ ኅሩይ ቅዱስ ጳውሎስ እንደነገረን›› (ኤፌ. ፪፥፲) ።

አገልግሎት ምንድን ነው?

አገልግሎት በአንድ ቃል ሊወሰን የማይችል ሰፋ ያለ ሐሳብ ነው። አገልግሎት አንድ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ጋር የሚያደርገው ጉዞ ነው። በክርስቶስ ኢየሱስ ያመነውን እምነት፣ በሐዋርያት የተሰበከለትን ወንጌል የሚኖርበት ሕይወት ነው። ክርስትና በቃልና በኑሮ የሚገለጽ ምስክርነት ነው። አገልግሎትም ይህን ሕይወት በመኖር ሌሎች ይኖሩት ዘንድ ብርሃንን መፍጠር ነው። አገልግሎት በሕይወት ላይ ክርስቶስን ንጉሥ አድርጎ መሾም ነው።

በዚህች ምድር ላይ እንኳ ብዙ ዓይነት አገልግሎት ይስተዋላል። ሰው ለባልንጀራው የሚሰጠው አገልግሎት፣ ሰው ለገዢው የሚሰጠው አገልግሎት፣ ሰው ለማኅበረሰቡ የሚሰጠው አገልግሎት አለ። እነዚህ አገልግሎቶች ሥጋዊ አገልግሎቶች ቢሆኑም የኃጢአትን መንገድ እስካልቀላቀሉ ድረስ ሰውን በእግዚአብሔር ዘንድ የሚያስነቅፉ አይደሉም።

እኛ ግን ከነዚህ ሁሉ የሚበልጠውን አገልግሎት እናያለን። ይህም መንፈሳዊ አገልግሎት ነው። መንፈሳዊ አገልገሎት ልዩ ልዩ ነው። ሰው እንደየጸጋው እግዚአብሔርን የሚያከብርበት መንገድ ነው። አገልግሎት ፍቅር ነው፣ አገልግሎት ትሕትና ነው፣ አገልግሎት የንጽሕና ሕይወት ነው፣ አገልግሎት በቅድስና የሚከወን ነው፣ አገልግሎት የሕይወት መንገድ ነው።

አገልግሎት ፍቅር ነው

አገልግሎት ከሰው ልብ የሚፈልቀው ፍቅር የሚገለጽበት መንገድ ነው። ፍቅር እግዚአብሔር ዓለምን ለመፍጠሩ ብሎም በኋለኛው ዘመን ለማዳኑ ምክንያት የሆነ የመንፈስ ፍሬ ነው። ፍቅር የሕግ ሁሉ የበላይ ነው። በፍቅር ውስጥ መታዘዝ እና ርኅራኄ ይሰፍናሉ። ይቅርታ እና ምሕረት ጎልተው ይታያሉ። ፍቅር በልቡ ውስጥ ያለ ሰው እግዚአብሔርን ከፍርዱ ጽናት የተነሣ ሳይሆን ከፍቅሩ ኀያልነት የተነሣ ይፈራዋል።

አገልግሎታችን በእግዚአብሔር የሚያስነቅፈን እንዳይሆን በፍቅር ላይ የተመሠረተ ይሆን ዘንድ ግድ ነው። ለዚህ አብነት ይሆነን ዘንድ ጌታ የኤፌሶንን ቤተ ክርስቲያን የነቀፈበትን ምክንያት ማየት ይበቃል። ‹‹ዳሩ ግን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ የቀደመውን ፍቅርህን ትተሃልና›› (ራዕ.፪፥፬) እግዚአብሔር በአገልግሎታችን ውስጥ ፍቅርን ያይ ዘንድ ይወዳል።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ በተመላለሰበት ዘመን ያደረጋቸው ተአምራት በሙሉ መነሻቸው ፍቅር ነበር። አገልግሎት ለእግዚአብሔር እና ለመንግሥቱ ያለን ፍቅር ነጸብራቅ ነው።

የጥበብ መጨረሻ የተባለው ፍቅር ፍቅረ እግዚአብሔር እና ፍቅረ ቢጽ በመባል ለሁለት ይከፈላል።

ፍቅረ እግዚአብሔር

እግዚአብሔርን መውደድ የአገልግሎት ብቻ ሳይሆን የክርስትና ሕይወትም መሠረት ነው። እግዚአብሔር ለሙሴ ሕግን በሰጠው ጊዜ ከትእዛዛቱ መካከል አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ በፍጹምም ነፍስህ በፍጹምም ኀይልህ ውደድ የሚለው ዋነኛው ነው። እውነተኛ አገልጋይ እግዚአብሔርን በፍጹም ልቡ በመውደድ ሰዎች እግዚአብሔርን እንዲወዱት የሚያደርግ ነው። ፍቅር የአገልግሎት መለኪያም ጭምር ነው። ለሊቀ ሐዋርያት ለቅዱስ ጴጥሮስ ሦስት ጊዜ የቀረበው የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ ትወደኛለህን? የሚለው ጥያቄ እና የሐዋርያውን መልስ ተከትሎ የተሰጠው የአገልግሎት ኀላፊነት እግዚአብሔር የአገልግሎታችንን መጠን ለእርሱ ባለን ፍቅር ልክ ለመለካቱ ማሳያ ነው።

ፍቅረ ቢጽ

ይህ ዓይነቱ ፍቅር እግዚአብሔር ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ በማለት ያዘዘውን ትእዛዝ የምንፈጽምበት ፍቅር ነው። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ስለዚህችኛይቱ ፍቅር ‹‹ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና እርሱም፦ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የሚል ነው›› በማለት ይነግረናል። ነገር ግን አንዳንድ ሰዎች ለእግዚአብሔር ያለን ፍቅር በቂ ሊሆን አይችልምን? ለሱ ያለን ፍቅር አገልግሎቱን ለመከወን በቂ ምክንያት አይደለምን? በማለት ሲጠይቁ ይስተዋላሉ፤ ይሁንና የፍቅር ሐዋርያ የተባለ ዮሐንስ እንዲህ በማለት ይመልስላቸዋል ጽድቅን የማያደርግና ወንድሙን የማይወድ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም። ዳግመኛም ሐዋርያው ወንድሙን የሚጠላ ሰው ከነፍሰ ገዳይ የማይለይ እንደሆነ፣ የዘላለም ሕይወት እንደሌለው እና የእግዚአብሔር ፍቅር በልቡ እንደሌለ ያረጋግጥልናል። (፩ኛ ዮሐ.፫፥፲፭-)

አገልግሎት ትሕትና ነው

ትሕትና የክርስቶስ ፍቅርና መሥዋዕትነት ነጸብራቅ ነው። በትሕትና ውስጥ የሕይወትን ትክክለኛ ትርጉም እና ወደ ዘለዓለማዊ ደስታ የሚወስደውን መንገድ እናገኛለን። አገልግሎት የእግዚአብሔር ትሕትና ማሳያ ነው። እርሱ እግዚአብሔር ሁሉን ሥራ በራሱ መከወን የሚችል የሚሳነው የሌለ አምላክ ሆኖ ሳለ ይህን የተቀደሰ አገልግሎት ለእኛ በመፍቀድ የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ተሳታፊ አደረገን። በመዋዕለ ሥጋዌውም ለፍጹም ትሕትና አብነት ሆነን። ‹‹ከእኔም ተማሩ እኔ የዋህ በልቤም ትሑት ነኝና››  በማለት ለትሕትና ጠራን።

የታመነ አገልጋይ ልቡ በቅንነት እና በትሕትና የተሞላ ነው፤ ወንድሙ ከእርሱ እንደሚሻል በትሕትና ያስባል። አገልግሎቱም ከንቱ ውዳሴን በመሻት የሚደረግ ሳይሆን የመንፈስ ፍሬዎችን ገንዘብ ያደረገ ይሆናል።

አገልግሎት የንጽሕና ሕይወት ነው

ንጽሕናን የምትሻ ነፍስ በመንፈስ ቅዱስ ለመሞላት የምትጠብቅን ዕቃ ትመስላለች። የእግዚአብሔር አገልጋይ ንጽሐ ልቡና ያለው ነውርና ነቀፋን የሚጸየፍ ነው። አገልግሎት ራስን ለእግዚአብሔር መስጠት ነው። እርሱ የሰጠንን ሀብት ለእርሱ መልሰን መሥዋዕት የምናደርግበት መንገድ ነው። ለእግዚአብሔር የሚቀርብ መሥዋዕት ደግሞ ንጹሕና የተመረጠ ይሆን ዘንድ ይገባል። ራሳችንን ለእግዚአብሔር ስናቀርብ በንጽሕና መሆን አለበት። መሥዋዕታችንም እንደ አቤል መሥዋዕት በአምላክ የተወደደ ይሆናል።

አገልግሎት በቅድስና የሚከወን ነው

እንደ እግዚአብሔር ያለ የቅድስና አስተማሪ ማነው? እንደ አምላካችን ያለ የሚያነጻ ማነው? እርሱ የሰውን ልጅ ለርኩሰት ሳይሆን ለቅድስና ጠርቶታልና። በአገልግሎታችን ሂደትም ይህን የተጠራንበትን ዓላማ ማክበር ይገባናል። ሰውነቱን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርጎ የሰጠ ሰው እግዚአብሔርን በቅድስና ያገለግል ዘንድ ግድ ነውና። አገልግሎት እግዚአብሔርን መስሎ ሌሎች እኛን ይመስሉ ዘንድ መጥራት ነው።  ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ በማለት እርሱን በቅድስናና በንጽሕና ወደመምሰል ይጠራናልና። እኛም እርሱን አብነት በማድረግ ለተቀደሰ አገልግሎት የተዘጋጀን መሆን አለብን።

አገልግሎት የሕይወት መንገድ ነው

አገልግሎት መንገድ ነው፤ ከአንደኛው ሰው ሕይወት ወደ ሌላኛው ሰው ሕይወት እየተሸጋገረ የሚቀጥል መንገድ። የሕይወትን እስትንፋስ ከአንዱ ወደ ሌላው እያዳረሰ የሚቀጥል ጥልቅ ጉዞ። ከሙሴ ወደ ኢያሱ የተሻገረ መንገድ፣ ከኤልያስ ወደ ኤልሳዕ የተሻገረ መንፈስ፣ ከጳውሎስ ወደ ጢሞቴዎስ የተሻገረ ጉዞ። አገልግሎት የሚቀጥል ነው። እግዚአብሔር ለቤቱ አገልጋይን ይተካል። ከትውልዱ መካከልም ብርቱውንና ደገኛውን ያስነሣል።

በእግዚአብሔር ቤት ስናገለግል በትምክህት እና በመታበይ የእግዚአብሔርንም ሕግ በመተላለፍ አይሁን። እግዚአብሔር አገልግሎታችንን ስንንቅ ለሚያከብሩት ይሰጣል። ኤሳው ብኩርናውን ንቆ ሸጠው፣ ያዕቆብ በረከቱን ወሰደ፤ ሳኦል በትዕቢት የእግዚአብሔርን ነቢይ አቃለለ ትእዛዙንም አፈረሰ፣ ዳዊት በትሕትናው ንጉሥ ሆነ፤ ይሁዳ ከክርስቶስ ደቀ መዝሙርነት ይልቅ የገንዘብ ፍቅር በለጠበት ከአገልግሎቱም ተሻረ፣ ስሙም ከሕይወት መዝገብ ተፋቀ፤ ማትያስ በትሕትና የሐዋርያነትን ጉዞ ተቀላቀለ።

ለዚህም አገልግሎታችን በፍቅር፣ በትሕትና፣ በንጽሕናና በቅድስና ያጌጠ፣ ለእግዚአብሔርም የተገባ ይሆን ዘንድ መትጋት አለብን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ኒቆዲሞስ

በዲ/ን ዮርዳኖስ ተክሉ

ኒቆዲሞስ መምህርና የአይሁድ መሪ ሆኖ ሳለ እውነትን ለማወቅ ከክርስቶስ ዘንድ ሊማር በሌሊት መጣ። ራሱን ዝቅ አድርጎ በመማር የትሕትና አርአያ ሆነ። ከዮሴፍ ጋር የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ በሐዲስ መቃብር በጌቴሴማኒ ቀበረ። እኛስ..???

በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ የዐቢይ ጾም የሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዐተ ማኅሌቱ በጾመ ድጓ መጽሐፍ ባዘጋጀው መሠረት የጾሙ ሰባተኛ ሳምንት ኒቆዲሞስ በመባል ይታወቃል።

በዚህ ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት፣ የሚነበበው ወንጌል “ኒቆዲሞስ”ን የሚያወሳ ነው። በዚህ ሰንበት በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት የተጻፈልን፦ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስ ለተባለ የአይሁድ አለቃ ያስተማረው ትምህርት፤ እንዲሁም የኒቆዲሞስ አስተማሪ መምህረ ትሕትና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስን ያስተማረው ትምህርት ይነበባል፣ ይተረጎማል፣ ይዜማል።

          ኒቆዲሞስ ግን ማን ነው?

ኒቆዲሞስ የሚለው ቃል የግሪክ ቃል ሲኾን፤ ትርጉሙም “ድል ማድረግ” ወይም “አሸናፊነት” ማለት ነው። ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ፣ የአይሁድ ሸንጎ አባል የነበረ ከአይሁድ አለቆችና መምህራን አንዱ ነው። (“ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤…” ዮሐ.፫፥፩)

ኒቆዲሞስ መምህር ሲሆን ራሱን ዝቅ አድርጎ የተማረ የትህትና አርአያ ነው። ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ ብቻ ሳይሆን የፈሪሳውያን አለቃ፣ የኦሪት መምህር ብቻ ሳይሆን የኦሪት ምሁርም ነበር። በእርሱ ደረጃ የነበሩ ታላላቅ የአይሁድ ምሁራን መንፈሳዊ ሥልጣናቸውና ሹመታቸው የእግዚአብሔር ስጦታ መሆኑን ረስተው በሕዝቡ ላይ የሚመጻደቁ ነበሩ። በዘመናቸው ዕውቀትን የሚገልጥ እውነተኛ አምላክ፣ የካህናት አለቃ ኢየሱስ ክርስቶስ ለቤዛ ዓለም ሲገለጥ የአይሁድ ምሁራን የጌታን መገለጥ አልወደዱትም። የእርሱ ትሕትና የእነርሱን ትዕቢት የሚያጋልጥ ነበርና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚሄዱትን ሁሉ ይነቅፉ ይከስሱ ነበር። ጌታችንም የፈሪሳውያን አሳባቸው በግብዝነት የተሞላና ከንቱም እንደሆነ ነግሯቸዋል። ለደቀ መዛሙርቱም ከጻፎችና ከፈሪሳውያን ጽድቅ የሚበልጥ ሥራን እንዲሠሩ አስጠንቅቋቸዋል። (“እላችኋለሁና፦ ጽድቃችሁ ከጻፎችና ከፈሪሳውያን ጽድቅ ካልበለጠ፥ ወደ መንግሥተ ሰማያት ከቶ አትገቡም።” ማቴ.፭፥፳፤ “ኢየሱስም፦ ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠንቀቁና ተጠበቁ አላቸው።” ማቴ.፲፮፥፮) ኒቆዲሞስ ከእነዚህ ከፈሪሳዊያን መካከል የተገኘ ልዩ ምሁረ ኦሪት ነበር።

የሌሊቱ ደቀ መዝሙር ኒቆዲሞስ

ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊና የአይሁድ ከፍተኛ ሸንጎ አባል ቢሆንም፣ በልቡ ግን እውነትን የማወቅ ከፍተኛ ጥማት ነበረው። ኒቆዲሞስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያደርጋቸውን ተአምራት ሲያይ፣ እሱ ከእግዚአብሔር ዘንድ የመጣ መሆኑን አመነ። ነገር ግን የአይሁድ መሪዎችን በመፍራት በግልጽ ሊከተለው አልደፈረም። ስለዚህ በሌሊት ወደ ጌታ መጣ።

ኒቆዲሞስ ራሱን ለእውነት፣ ልቡን ለእምነት አዘጋጅቶ ከዅሉ ቀድሞ በሌሊት ክርስቶስን ፍለጋ የመጣ ከእነዚህ ፈሪሳዊያን ወገን ተለይቶ እንደ አባታችን አብርሃም ወደ ጽድቅ መንገድ የተጠራ ነው። ኒቆዲሞስ ሹመት እያለው፤ ዕውቀት እያለው፤ ሀብት እያለው ሁሉ ሳይጎድልበት እውነትን ለማወቅ እልቅናው ሳይታሰበው ከአካባቢው ጋር መመሳሰልን ሳይመርጥ ራሱን ዝቅ አድርጎ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሊማር በሌሊት መጣ። መምህረ ትሕትና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የኒቆዲሞስን ትሕትናውን ተቀብሎ “ለምን በቀን አትመጣም?” ሳይለው እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ትውልድ ሁሉ የሚማርበትን ረቂቁን ምሥጢር “ምሥጢረ ጥምቀት”ን አስተማረው፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም” (ዮሐ.፫፥፫) አለው። ኒቆዲሞስ መጀመሪያ ነገሩ ግራ ገብቶት “ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?” (ዮሐ.፫፥፬) ብሎ ጠይቆ ነበር። ጌታም ልደቱ ከሥጋ ሳይሆን “ከውኃና ከመንፈስ” (በጥምቀት) መሆኑን አስረዳው፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም” (ዮሐ.፫፥፭)።

ለምን ይሆን ኒቆዲሞስ ከቀኑ ክፍለ ጊዜ ይልቅ የሌሊቱን ጊዜ ለትምህርት የመረጠው ?

ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነው ኒቆዲሞስ ቀን ቀን በአይሁድ ወንበር በሸንጎ እየዋለ ሌሊት ሌሊት ደግሞ ጌታችን ዘንድ እየመጣ ቃለ ወንጌልን ይማር ነበር። ከጌታችን ዘንድ ለመማር ሌሊቱን የመረጠበትም ምክንያት እነሆ፦

፩- የአይሁድ መምህር ስለነበር ስማር ብዙ ሰዎች ሲያዩኝ በውዳሴ ከንቱ መምህር መባል ይቀርብኛል ብሎ፤ እንዳያዩት ፈርቶ ሌሊት እየመጣ ይማር ነበር።

፪- ከቀን ልብ ይልቅ የሌሊት ልብ የተካተተ ስለሆነ በሙሉ ልቡ በማስተዋል ለመማር ስለፈለገ ከቀኑ ክፍለ ጊዜ ይልቅ የማታውን መረጠ።

፫- ሌሊት ጨለማ ነው፤ ብርሃን የለም ጨለማ የኃጢአት ምሳሌ ነው። ኒቆዲሞስ በሌሊት መምጣቱ በኃጢአት እንዳለ ንስሐ እንደሚፈልግ የሚያስረዳን ነው።

፬- ሌሊት የብሉይ ኪዳን ምሳሌ ነው። ኒቆዲሞስም “እኔ ምሁረ ኦሪት እንጂ ምሁረ ወንጌል አይደለሁም። ወንጌልን ካንተ እማር ዘንድ ያስፈልገኛል” ሲል በሌሊት ይመጣ ነበር።

ኒቆዲሞስ ከጨለማ ተማሪነት ወደ ብርሃን ምስክርነት

የኒቆዲሞስ ታሪክ አንድ ሰው ከጥርጣሬና ከፍርሃት ወጥቶ እንዴት የክርስቶስ እውነተኛ ምስክር ሊሆን እንደሚችል የሚያሳይ ትልቅ ትምህርት ነው።

ኒቆዲሞስ በልቡ ያደረው የጌታ ፍቅር እያደገ ሲመጣ፤ አይሁድ ጌታን ያለ ጥፋቱ ሊይዙትና ሊፈርዱበት በሚያሴሩበት ጊዜ፣ በሸንጎው መካከል በድፍረት ቆሞ፦ “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” (ዮሐ.፯፥፶፩) በማለት ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሟገተ። ይህ የሚያሳየው ኒቆዲሞስ ቀስ በቀስ ከፍርሃት እየወጣና ለጽድቅ/ለእውነት መቆም እየጀመረ እንደነበር ነው።

የዕለተ ዓርቡ ታላቅ ምስክርነት

የኒቆዲሞስ እውነተኛ ፍቅርና ድፍረት በጉልህ የታየው ጌታችን በተሰቀለበት ዕለት በዕለተ ዓርብ ነው። ደቀ መዛሙርቱ በፈሩበትና በሸሹበት በዚያ አስጨናቂ ሰዓት፣ ኒቆዲሞስ ግን ፍርሃቱን አስወግዶ ማንነቱን በግልጽ አሳወቀ።

ኒቆዲሞስ ከጌታችን በተማረው ትምህርት ጸንቶ ለመኖር የበቃ ታላቅ አባት ነው። የሃይማኖቱ ጽናትም በተግባር የተፈተነ ነው። ለዚህም ማሳያ የሚሆነን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለ ጊዜ የአርማትያስ ሰው ከሚሆን ከዮሴፍ ጋር በመሆን የአይሁድን ድንፋታ ሳይፈራ “እሱን ያገኘ ያገኘኛል” ሳይል በድፍረት የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውን ከጲላጦስ ለምኖ፤ መቶ ንጥር የሚያህል የከርቤና የእሬት ቅልቅል ይዞ መጥቶ (በወቅቱ ይህ በጣም ውድና ለነገሥታት ክብር የሚቀርብ ሽቶ ነበር)፤ ከዮሴፍ ጋር የጌታን ቅዱስ ሥጋ በንጹሕ የተልባ እግር በፍታ ከሽቶ ጋር ገነዙት፤ በጌቴሴማኒም በአዲስ መቃብር ቀበሩት።

የጌታችንን ክቡር ሥጋ ገንዘው ሲቀብሩም በጸናች የተዋሕዶ እምነት ጌታችን እንደገለጠላቸው “ቅዱስ እግዚአብሔር፣ ቅዱስ ኃያል፣ ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት…” የሚለውን ጸሎት እስከ ፍጻሜው እየጸለዩ ነበር። በዚህም ኒቆዲሞስ ከሐዲስ ኪዳን ካህናት ቀድሞ ምሥጢረ ጥምቀትን ከጌታ እንደተማረ፣ የሐዲስ ኪዳንን የምሥጢራት አክሊል ምሥጢረ ቁርባንንም እንዲሁ ተማረ። ይህንንም በሚመለከት ሊቁ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ አብሮት ይቀድስ የነበረውን ንፍቅ ካህን በባረከበት አንቀጽ “በዚህ ምሥጢር እየተራዳኝ ከእኔ ጋር ያለ ይህንን ካህን እርሱንም እኔንም ሥጋህን እንደገነዙት እንደ ዮሴፍና እንደ ኒቆዲሞስ አድርገን” እንዲል (ቅዳሴ ማርያም ቁጥር ፻፲፭/115)።

በሌሊት ተደብቆ የመጣው ኒቆዲሞስ፣ በመጨረሻ በፀሐይ ብርሃን ለዓለም ሁሉ በሚታይ ሁኔታ የጌታ አገልጋይ መሆኑን በተግባር አረጋገጠ።

እኛስ ዛሬ እንደ ኒቆዲሞስ እውነተኛ የክርስቶስ ወዳጆች ለመሆን ምን ያስፈልገናል?

‎ከኒቆዲሞስ ታሪክ የምንማራቸው ሰባት(፯) ዋና ዋና ነጥቦች፦

፩- ፍርሃትን ማሸነፍ (ከሌሊት ወደ ብርሃን መውጣት)

ኒቆዲሞስ መጀመሪያ አካባቢ “ሰው ምን ይለኛል?” ብሎ በመፍራት በሌሊት ነበር የመጣው። እኛስ ዛሬ በጓደኞቻችን ወይም በቤተሰባችን ዘንድ ላለመናቅ ብለን የምንደብቀው በጎ ማንነት ወይም እምነት አለን?

ስለአንዲቱ ሃይማኖታችን ቆመን ለመመስከር መጀመሪያ በውስጣችን ያለውን የሰው ፍርሃት በእግዚአብሔር ፍቅር መተካት ያስፈልገናል (ከጨለማ ወደ ብርሃን እንውጣ)።

፪- ትኅትና፦ ኒቆዲሞስ ትልቅ ምሁርና መሪ ቢሆንም፣ ያላወቀውን ነገር ለመማር በጌታ እግር ሥር ተደፍቷል። እርሱ መምህር ቢሆንም ጣት ከጣት እንደሚበልጥ ከመምህር መምህር ይበልጣና ለመማር በትኅትና ወደ ክርስቶስ ሄደ በዚያች ትሕትናውም መምህር ፍለጋ ሄዶ አምላኩን አገኘ፤ የሕይወትንም ቃል ሰማ። ስለዚህ እኛም እንደኒቆዲሞስ የሕይወትን ቃል እንሰማ ዘንድ ትኅትናን ገንዘብ ልናደርግ ይገባናል።

፫- የማወቅ ፍላጎት (ለትምህርት ጊዜ መስጠት)

ኒቆዲሞስ ምንም እንኳን የቀኑ ክፍለ ጊዜ ባይመቸውም በሌሊቱ ሰዓት ለመማር ችሏል፤ እኛም  ከእሱ ተምረን “ከልብ ካለቀሱ ዕንባ አይገድም” እንዲሉ ምንም ሥራ ቢበዛብን ቅዱስ ቃሉን የምንማርበት ጊዜ አይጠፋምና ሕይወት ለሚገኝበት ትምህርት ጊዜ ልንሰጥ ይገባናል።

፬- እድገት/ለውጥ፦ ኒቆዲሞስ በእምነቱ እያደገ እንደሄደ ማለትም ከሌሊት/ ከፍርሃት ተነሥቶ እስከ ቀራንዮ አደባባይ/መስቀል ሥር እንደደረሰ፤ እኛም በእምነታችን ጠንክረን ባለንበት ቦታና ሁኔታ ሁሉ ያለፍርሃት እስከሞት ድረስ ስለአንዲቱ ሃይማኖታችን ልንመሰክር ይገባናል።

፭- እውነትን በድፍረት መናገር (በሸንጎው ፊት መቆም)

ኒቆዲሞስ አይሁድ ጌታን ያለ ጥፋቱ ሲከሱት “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” (ዮሐ.፯፥፶፩) ብሎ ተከራክሯል። እኛስ ጓደኞቻችን አንድን ሰው ያለአግባብ ሲያሙ ወይም ሲሳለቁ አይተን “ይህ ስህተት ነው” ብለን የመገሰጽ ድፍረት አለን?

እውነተኛ ክርስቲያን ማለት አብዛኛው ሰው ስህተት በሆነ መንገድ ሲጓዝ፣ እርሱ ብቻውን ቢሆንም እንኳ በእውነት መንገድ ላይ በመጽናት የሚጓዝ ነው።

፮- መሥዋዕትነት (ምርጥ ስጦታን መስጠት)፦ ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር በንግግር ብቻ ሳይሆን በዕለተ ዓርብ እንደታየው በሕይወታችን፤ በጊዜያችንና በንብረታችን መስዋዕትነት ከፍለን መግለጽ ይገባናል። ኒቆዲሞስ ለጌታ ቀብር እጅግ ውድ የሆነ ሽቶ ይዞ መጥቷል። እኛ ለፈጣሪያችንና ለሰዎች የምንሰጠው “ውድ” የምንለው ነገር ምንድን ነው? ወይስ የተረፈንን ብቻ ነው የምንሰጠው?

እውነተኛ ሃይማኖት ከመሰጠትና ከመስጠት ጋር የተያያዘ ነው። ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን እስከሞት ድረስ አሳልፎ በመስጠት እንደወደደን፤ እኛም በፍጹም ፍቅር ራሳችንን አሳልፈን ልንሰጠው ይገባናል። ለሰዎች/ለባልንጀሮቻችን ደግሞ እንደራሳችን አድርገን ወድደናቸው፤ ለእኛ የሚያስፈልገን ሁሉ ለእነርሱም ያስፈልጋቸዋልና ካለን ላይ ልንሰጣቸው ይገናባል።

፯- በመከራ ጊዜ አለመሸሽ (በመስቀሉ ሥር መገኘት)

ብዙዎች ጌታን ጥለውት በሸሹበት ሰዓት ኒቆዲሞስ ግን በግልጽ ወጥቶ ሥጋውን ተቀብሏል። እኛስ ነገሮች ሲበላሹና መከራ ሲመጣ በጽናት እንቆማለን ወይስ እንደ ደቀመዛሙርቱ እንሸሻለን?

እውነተኛ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን የሚታወቀው በደስታ ጊዜ ብቻ ሳይሆን በፈተና ወቅት በሚያሳየው ታማኝነት፤ በመከራ ጊዜ ስለሃይማኖቱ በሚያደርገው ተጋድሎ (ሰማዕትነት)ነው።

‎‎ኒቆዲሞስ ጉዞውን በጥያቄ ጀምሮ በእምነትና በተግባር ጨረሰ። እኛም ዛሬ የክርስትና ሕይወታችን ከቃላት አልፎ በተግባር የተገለጠ እንዲሆን እነዚህን የኒቆዲሞስን ጠንካራ ጎኖች ልንላበስ ይገባል። ለዚህም አምላከ ኒቆዲሞስ ብርታቱንና ጽናቱን ያድለን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር

«መጽአ ኀበ እግዚእ ኢየሱስ ቀዲሙ ሌሊተ፣ አስቀድሞ በሌሊት ወደ ጌታ ኢየሱስ መጣ።»

የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት ቁጥር አንድ (፫፥፩) ላይ ይህንን ሃሳብ እናገኛለን፡፡ በዚህ ርዕስ ማን እንደመጣ፣ ለምን እንደመጣ እንመለከታለን፡፡ የመጣው በምዕራፉ መጀመሪያ ላይ እንደምናገኘው ኒቆዲሞስ ነው፡፡

ኒቆዲሞስ ፡- የዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት ገልጠን ስናነብ «ከፈሪሳውያን ወገን የነበረ የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፡፡» እያለ ስሙ እስከነ ወገኑና ሙያው ይነግረናል፣ ወገኑን የመግለጡ ነገር ለምን ይሆን ብለን ከጠየቅን ቀጥሎ   «በሌሊት ወደ ጌታ መጣ።» የሚለው ነውና በምን ዓይነት አኳኋን ወደጌታ መምጣቱ፣ ያለበትን ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጫና እንድንረዳ ነው።

ከፈሪሳውያን ወገን መሆኑን ብቻ የነገረን ሳይሆን የእነርሱ አለቃቸው እንደሆነም ጭምር ሲገልጥልን፣ ሊቃውንት ሲበይኑት ምሁረ ኦሪት (ዮሐ. ፫፥፲) እንዲሁም ባዕለ ጸጋ መሆኑን ያስረዳሉ።

አንድምታ ወንጌል «በሌሊት ወደ ጌታ ኢየሱስ መጣ» የሚለውን«ከመዓልት ከሚመጡት አስቀድሞ»፣ አንድም « ከማመን አስቀድሞ» የሚለውን አስቀድሞ በማለት የኒቆዲሞስ የአመጣጥ ሁኔታውን ይነግረናል።

ኒቆዲሞስ ቀድመን እንዳየነው ከፈሪሳውያን ወገን የሆነ ሰው ነው፤ የአይሁድ የሸንጎ ዳኛ ነው፤ ስለሆነም ከፈሪሳውያን ወገን እንደመሆኑ ፍርሀት አለበት፤ የአይሁድ የሸንጎ ዳኛ እንደመሆኑ ቀን ቀን የዳኝነት ሥራው በችሎት ሲፈርድ፣ ሕግ ሲያወጣ ሲያረቅ፣ ሲያስፈጽም፣ ሲያስታርቅ… ይውላል፤ ያለው ብቸኛ አማራጭ ደግሞ የሌሊት ጊዜውን በአግባቡ መጠቀም ነውና ሌሊት ከሰማያዊ ዳኛ፣ ንጉሥ፣ ባእለ ጸጋ ኢየሱስ ዘንድ ሊማር ወስኖ ተነሣ።

«ሀቡ ዘቄሳር ለቄሳር ወዘእግዚአብሔር ለእግዚአብሔር፤ የቄሳርን ለቄሳር፣ የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ስጡ።» እንዳለው ጌታ በወንጌሉ (ማቴ. ፳፪፥፲፯) ለሥራው፣ ለአመራሩ የሚገባ ጊዜ ከሰጠ በኋላ ለመንፈሳዊ ሕይወቱ (ለእግዚአብሔር) መስጠት ያለበትን ጊዜ መስጠቱን እንገነዘባለን፡፡

መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም ኒቆዲሞስን « የማታ ተማሪ፤ Extension student» በማለት ይጠሩታል፤ ይህም ማለታቸው ከዘመናችን በማስተያየት ነው። ይህንን ንጽጽር የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ልብ ልትሉት የሚገባ ነጥብ ነው፤ ምክንያቱም ቀን ቀን አመዛኙ ጊዜያችሁን ለአስኳላ ትምህርታችሁ ትሰጣላችሁ፣ የሌሊት ጊዜያችሁ ደግሞ ለመንፈሳዊ ሕይወታችሁ ለሆነው ለቃለ እግዚአብሔርና ለመንፈሳዊ አገልግሎት ትሰጣላችሁና ነው።

በዚህ ልክ ጊዜያችንን ከፋፍለን የማንጠቀም ከሆነ ግን ሙሉ ሰው አንሆንም ማለት ነው። ምክንያቱም ምሉዕነት የሚገኘው ቢያንስ ፈቃደ ሥጋ ከፈቃደ ነፍስ በተዐቅቦ(በመጠባበቅ) መኖር ሲችሉ፣ ቢቻል ግን በፍጹምነት ሥጋ በነፍስ ግዛት ሥር ሆና መኖር ስትችል ነውና፡፡

በሌሊት የሚመሰሉት የሚከተሉት ነጥቦችን እንመልከት

አንደኛ ዘመነ ብሉይ ነው፤

” ከግላ ኦሪት አልተላቀቀም…” እንዲል አንድምታ ወንጌል፣ ሌሊት ማለት የተከደነ የተሸፈነና ጨለማ ማለት አንደሆነ ይታወቃል። “ገለወ/ሸፈነ” እንደሚለውም “ግላ” ማለት የተከደነ የተሸፈነ ማለት ነው፤ መሸፈኑም መከደኑም አልያም ጨለማነቱም ሰው በበደሉ ምክንያት የጨለማ ገዥ በሆነው በዲያብሎስ ግዞት ሥር “አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ፣ ሔዋን አመቱ ለዲያብሎስ፤ አዳም የዲያብሎስ ወንድ ባርያ ሔዋን የዲያብሎስ ሴት ባርያ” በመሆኑና የጨለማ ሥራ እየሠራ ከአምልኮተ እግዚአብሔር መለየቱ ነው። በወቅቱ ኃጢአት በምድር ላይ በምልዐት ሆነ [ኵሉ አረዩ ወኅቡረ አለው…፤ ሁሉ ዐመፁ በአንድነትም ረከሱ፤ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ የለም” እንዲል ዳዊት በመዝሙሩ (መዝ. ፲፬፥፫) በፍዳ የተያዝንበት ወቅት ነበረ።

“ሕዝብ ዘይነብር ውስተ ጽልመት ወጽላሎተ ሞት ብርሀን ዐቢይ ሠረቀ ላዕሌሆሙ፤ በጨለማ የተቀመጠው ሕዝብ ታላቅ ብርሃን አየ፥ በሞት አገርና ጥላ ለተቀመጡትም ብርሃን ወጣላቸው።” (ኢሳ. ፱፥፪፣ ማቴ. ፪፥፲፬-፲፮) እንደ ተባለው ጨለማ የተባለው ዘመነ ብሉይ ታላቅ ብርሀን በተባለው በዘመነ ሐዲስ ተተካ፣ “በሌሊት ይደምፅ ብካይ ወበጽባሕ ፍሥሐ፤ ልቅሶ ማታ ይመጣል፥ ጠዋት ግን ደስታ ይሆናል።” (መዝ. ፴፥፭)

በብሉይ ልቅሶ ነበር፤ ” ነባይነ ነባይነ ከመ ዘኢነባይነ ኮነ፤ ጮህን ጮህን እንዳልጮህን ሆንን” እንዲል የገዐር የጩኸት ዘመን ነበር።

በሌሊት ትግል አለ። አበው ብሕትውናን ሲገልጹት “ግርማ ሌሊቱን ፀብአ አጋንንቱን ታግሰው” እንዲሉ ትግል፣ ፍርሃት፣ እንግልት፣ ሥቃይ… ያለው በሌሊት ነው። ለዚህ ነው ያዕቆብ ከእግዚአብሔር ሲታገል እግዚአብሔር “ሊነጋ አቅላልቶአልና ልቀቀኝ።” ያለው (ዘፍ. ፴፪፥፳፮) ሌሊት የተባለው እንደ ጥንቱ ትርጓሜ መጽሐፍ ዘመነ ብሉይን ነው፤ ኒቆዲሞስም ገና በሕገ ኦሪት ሳለ መዓልት ወንጌልን ሳያይ በፈሪሳውያን የጭንቅ ሕግ ቀንበር ላይ እያለ ነው ወደ ጌታ የመጣው።

ሁለተኛ አለማወቅን ነው።

ኒቆዲሞስ የሐዲስ ኪዳን ትምህርት ሳይማር ሳይረዳ ለመማር ወደመምህር መጣ። በዚህም የተነሳ የሐዲስ ኪዳን መመስረቻ የሆነውን ምሥጢረ ጥምቀትን ተማረ።

ሦስተኛ ይህንን ዓለም ነው።

ምድራዊ ሕይወት የቀቢጸ ተስፋ፤ የተስፋ መቁረጥ ጨለማ የሰፈነበት፣ የፈተና እንቅፋት የተቀመጠበት በመሆኑ በሌሊት ይመሰላል። በሌሊት የሚሄድ ሰው እንደሚሰናከል እንደዚሁ በዚህ ዓለም መሰናክል አለ። ክርስቲያን ደግሞ እነዚያ መሰናክሎችን አልፎ ነው በጌታ፣ በቀንና በብርሀን በተመሰለው በመንግሥተ ሰማይ ከክርስቶስ ጋራ መቆም የሚችሉት።

አራተኛ አለማመንን ነው።

አለማመን ጨለማ(ሌሊት) ነው፤ ማመን ደግሞ ብርሀን(ቀን) ነው፤ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሁም ልጅነት በምታሰጥ ጥምቀት አጠቃላይ በሐዲስ ኪዳን ትምህርት ከማመኑ በፊት በኦሪት እምነት እያለ መጥቷልና።

አምስተኛ መከራ ነው።

ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገንና የአይሁድ አለቃ እንደመሆኑ ወደ ጌታ ዘንድ መሄድ ለእርሱ ሕጉ እጅግ ይበረታበታል፤ ማለትም አይሁድ በሸንጓቸው በመካከላቸው ወደጌታ ኢየሱስ ዘንድ የሚሄድ ሰው ቢኖር ከምኩራብ እንዲሰደድ የሚል ድንጋጌ ስለደነገጉ ማለት ነው፤ እርሱ ደግሞ የሸንጎው ዳኛ እንደመሆኑ ሕጉ ይጸናበታልና ነው። በዚህም እኛ የምንማረው በመከራ፣ በኃዘን፣ በችግር ሳለን መፍትሔ ወደሚሰጠን ጌታ ዘንድ መሄድ እነዳለብን ነው

ኢየሱስ: – “ወንጌል ክርስቶስ፣ ክርስቶስ ተስፋ፣ ተስፋ መንግሥተ ሰማያት” እንዲል አንድምታ ወንጌል፣ ንጋት የተባለው ወንጌል ያየንበት ሌሊት ብሉይን ያመለጥንበት እርሱ ኢየሱስ “ፀሐየ ጽድቅ” ነው። አካላዊ ቃል፣ መለኮትና ሥጋ በተዋሕዶ ለድኅነተ ዓለም ሰው ሆኖ በተገለጠ ጊዜ ኒቆዲሞስን ሲያገኘው አዲስ ሥርዓት ምሥጢረ ጥምቀትን (ረቂቅ ልደትንና) ሰማያዊ ዕውቀትን አስተማረው።

ይህንን ሰማያዊ ጥበብ እንደሚያስተምረውም አውቆ የአይሁድ መምህር ኒቆዲሞስ ተደብቆ “በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጣ” አለ።

“መጣ” አለ ከልቡ ጽድቅን ሽቶ አእምሮ በሚሰበሰብበት ጊዜ ሌሊት መጥቷልና፤ በፍጹም ትሕትና ሊሰግድለት መጥቷልና፤ ሥጋዊውን ምስፍና አቃሎ ለአገልጋይነት መጥቷልና፤ ለምስክርነት መጥቷልና፤ “መምህር ሆይ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን አለው።” እንዲል ወንጌሉ መስክሮለታል (ዮሐ. ፫፥፪) በዚህም ክርስቶስ “እውነተኛ መምህር” እንደሆነ አስረዳን።

“ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ መጣ” ሲል ገንዘብን፣ ሥልጣንን ወይም ሌላ ምድራዊ ጥበብን ፈልጎ ሳይሆን ሰማያዊ ሀብትን ብቻ ፈልጎ ስለመጣ አመጣጡ ልዩ ያደርገዋል። ወደኋላም ባለመመለስ ምድራዊ ሹመትን፣ ሽልማቱን ዝናውን ሁሉ ጥሎ እስከ መስቀል ታምኖ ከዮሴፍ ጋር የጌታችን ቅዱስ ሥጋውን ገንዟል። “…ዮሴፍ ወኒቆዲሞስ ገነዝዎ ለኢየሱስ፤ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ኢየሱስን ገነዙት” እንዲል (ዮሐ ፲፱፥፴፰-፴፱)

“ቃሉን ስበክ፥ በጊዜውም አለጊዜውም ጽና።” ፪ኛ ጢሞ. ፬፥፪ እንዳለው እናንተ የግቢ ተማሪዎች ኒቆዲሞስን አብነት አድርጋችሁ የጥበባት ሁሉ ምንጭ የሆነው ዕውቀት የሰጣችሁ እንዲሁም የሚሰጣችሁ አምላካችንን ፈልጋችሁ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መምጣት ይኖርባችኋል፤ ኒቆዲሞስ ምሁረ ኦሪት ሲሆን ፍጹም ዕውቀት የሚገኘው ከአምላክ እንደሆነ ዐውቆ መጥቷልና። በመምጣቱም ሳይንስ በላቦራቶሪና በምጡቅ ቴክኖሎጂው ፈላስፋዎች ደግሞ በፍልስፍናቸው የማይደርሱበት የዳግም ልደት ምሥጢርን ገለጠለት።

ምሁራን እንደሚያስረዱን የእውቀት ምንጭ /source of knowledge የሚባሉት ሦስት ናቸው። እነዚህም ሳይንስ፣ ፍልስፍና እና ቲኦሎጂ ሲሆኑ ከሁሉ የሚበልጠው ደግሞ የነገረ መለኮት ትምህርት ነው። ምክንያቱም ሳይንስና ፍልሰፍና የሚመረምሩት በአምስቱ የስሜት ሕዋሳቶች ተመርምረው የሚደረስባቸውን ብቻ ነው፤ ማለትም ግዑዙን ዓለም ብቻ ነው፣ ሥጋን እንጂ ነፍስን፣ መንፈስን ፣መልአክንና አምላክን መመረመር አይችልም፤ ስለ ሞትና ከሞት በኋላ ስላለው ሕይወት ስለ ምድር እንጂ ስለሰማይ መረዳት አይችልም፤ ስለ ምድራዊውም ቢሆን ያለው መረዳትና ግንዛቤ ተከፍሎ/partiality አለበት፤ ቋሚ መረዳት የለውም፤ ዥዋዥዌ ሆኖ ሁሌ ይዋዥቃል። ጥናቱም ሲሰራ አንዱ በጥናቱ ያገኘውን ግኝት/finding ሌላው አጥኚ እንደገና አጥንቶ ሊያፈርሰው ይችላል። ጥናትን የሚያፈርስ ጥናት/antithesis ይሠራል።

ፊሎሶፊም ቢሆን ከሳይንስ አንድ ደረጃ ከፍ ብሎ ሜታፊዚክስ/metaphysics በሚለው ዘርፍ ውስጥ ከቁስ ውጪ ያሉትን አጠናለሁ ቢልም የሚያጠናበት መሣሪያው በቦታ የሚወሰንና ገደብ ያለበት የሰው አእምሮ በመሆኑ የሚወሰን አካል/finite being ለማይወሰን አካል/ infinite being መመርመር አይችልምና ከሚታየው ዓለም ውጪ አልፎ ረቂቁን መገንዘብ አይችልም።

ነገረ መለኮት ግን የዕውቀቱ መሠረት ራሱ እግዚአብሔር ሆኖ በመገለጥ(revelation) ሥርዓት ስለሆነ ምንም የሚሠወር ነገር አይኖረውም። ግዑዙ ረቂቅን መመርመር ቢያቅተው እንጂ ረቂቁ ግዑዝ አካልን መመርመር አይሳነውምና፤ አምላክ በዕውቀት ተከፍሎ የሌለበት ሁሉን አዋቂ/ omniscient ነውና፤ ሁሉን አዋቂ አምላክ ደግሞ ለሰው ልጅ ከጥንት ጀምሮ ዕውቀትን ሲገልጥ ቆይቷል። ሐዋርያው በዕብራውያን መልእክቱ «ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን፤» እንዳለ። (ዕብ. ፩፥፩

ሁለት ዓይነት መገለጥ መኖሩን የነገረ መለኮት ምሁራን ያስቀምጣሉ የመጀመሪያው ዓቢይ መገለጥ (general revelation) ሲሆን የሁለተኛው ንኡስ መገለጥ (specific revelation) ይባላል። ንኡስ መገለጥ የሚባለው «ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናገረ።» ያለውን ሲሆን፤ ዓቢይ መገለጥ የሚባለው ደግሞ «ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን፤» የሚለው ነው። በዚህ በሁለቱ መገለጥ ሳይንስና ፍልስፍና በእውናቸው ይቅርና በሕልማቸው የማያስቡት ምሥጢር ተገልጧል።

 በመሆኑም ያላችሁን ጊዜ በአግባቡ ተጠቅማችሁ መንፈሳዊ ዕውቀትን ልትቀስሙ ኒቆዲሞስንም አብነት በማድረግ በግቢ ጉባኤ አገልግሎት ሱቱፋን ሆናችሁ መገኘት ይኖርባችኋል።

ወርኃ መጋቢት ፳፻፲፰ ዓ/ም

መ/ር አበበ ፍቅሬ

ቃና ዘገሊላ

ይህ በዓል ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከዘጠኙ ንዑሳን በዓላት መካከል አንዱ ሲሆን ይህም ጥር ፲፪ቀን ይውላል፡፡ የቃና ዘገሊላ ጥንተ ነገሩ ወይም ታሪኩ የተፈፀመው የካቲት ፳፫ ቀን ነው፡፡ ነገር ግን አባቶቻችን የውኃን በዓል ከውኃ በዓል ጋር ለማክበር ብለው የየካቲቱን በዓል ወደ ጥር ፲፪ አምጥተውታል፡፡ ይህም ውኃ ወደ ወይን የተለወጠበትን በዓል ከጌታ ጥምቀት በዓል ጋር በማስተሳሰር ለማክበር ነው፡፡ (ስንክሳር ዘጥር ፲፪)

“በሦስተኛውም ቀን በገሊላ ቃና ሠርግ ነበረ፥ የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች፤ ኢየሱስም ደግሞ ደቀ መዛሙርቱም ወደ ሠርጉ ታደሙ። የወይን ጠጅም ባለቀ ጊዜ የኢየሱስ እናት፡- “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” አለችው። ኢየሱስም፡- “አንቺ ሴት፥ ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም” አላት። እናቱም ለአገልጋዮቹ፡- “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ” አለቻቸው። አይሁድም እንደሚያደርጉት የማንጻት ልማድ ስድስት የድንጋይ ጋኖች በዚያ ተቀምጠው ነበር፥ እያንዳንዳቸውም ሁለት ወይም ሦስት እንስራ ይይዙ ነበር። ኢየሱስም፡- “ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው” አላቸው። እስከ አፋቸውም ሞሉአቸው። “አሁን ቀድታችሁ ለአሳዳሪው ስጡት” አላቸው፤ ሰጡትም። አሳዳሪውም የወይን ጠጅ የሆነውን ውኃ በቀመሰ ጊዜ ከወዴት እንደ መጣ አላወቀም፤ ውኃውን የቀዱት አገልጋዮች ግን ያውቁ ነበር፤ አሳዳሪው ሙሽራውን ጠርቶ፡- ሰው ሁሉ አስቀድሞ መልካሙን የወይን ጠጅ ያቀርባል፥ ከሰከሩም በኋላ መናኛውን፤ አንተስ መልካሙን የወይን ጠጅ እስከ አሁን አቆይተሃል?” አለው። ኢየሱስ ይህን የምልክቶች መጀመሪያ በገሊላ ቃና አደረገ፤ ክብሩንም ገለጠ፥ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ።”(ዮሐ. ፪፥፩-፲፩)።

ሦስተኛ ቀን ምንድን ነው?

፩. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀው ጥር ፲፩ ቀን ነው፡፡ ወዲያውኑ እንደተጠመቀ ሳይውል ሳያድር ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሄደ፤ ፵ ቀንና ፵ ሌሊት ጾመ፤ ጾሙ የካቲት ፳ ቀን ቅዳሜ ይፈጸማል፡፡ ለእሁድ ሦስተኛ ቀን የካቲት ፳፫ ቀን ማክሰኞ በሦስተኛው ቀን ሠርግ ነበር፡፡

ሦስተኛ ቀን የሚለው፡-

  • የመጀመሪያ ቀን የሚባለው ዘመነ አበው፤ አዳም፤ እነአብርሃም፤ ይስሐቅ አበው የነበሩበት ዘመን ሲሆን፤
    •  ሁለተኛ ቀን የሚባለው ዘመነ ኦሪት ነው፤ እነሙሴ የነበሩበት ዘመን፣
    •  ሦስተኛ ቀን የተባለው ዘመነ ሐዲስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የሆነበት ዘመን ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ነበር ሠርግ የሆነው።

፪.ጌታችን  ፊልጶስን  አግኝቶ  “ተከተለኝ”  ካለበትና  ፊልጰስም  ጓደኛውን  ናትናኤልን  ከጠራበት  ዕለት  ሦስት  ቀን በኋላ ተአምሩን አደረገ  ነው፡፡ (ዮሐ. ፩፥፵፬) 

፫.በነገው ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ቆመው ነበር። ያለውን እሑድ (ዮሐ. ፩፥፴፭)፣ በነገው ኢየሱስ ወደ ገሊላ ሊወጣ ወደደ፥ ፊልጶስንም አገኘና ተከተለኝ አለው (ቁ.፵፬) ያለውን ሰኞ ብሎ በመተርጐም ማክሰኞ  ተአምሩን  በቃና  አደረገ  የሚል  ነው፡፡

፬. የእኛ ቤተ ክርስቲያን የበለጠ  የምታስተምረው አገባብ ደግሞ ጌታችን  በዮሐንስ  እጅ ከተጠመቀ በኋላ  ሳይውል  ሳያድር ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሔዶ የጾመውን ዐርባ ቀንና ሌሊት  እንደ  አንድ  ቀን በመቁጠር ከዚያ  መልስ  ተአምራቱን አደረገ  የሚል  ነው፡፡ (ቃና ዘገሊላ፤ ዲ/ን ሔኖክ ኃይሌ)

ዐርባ ቀንና ሌሊት እንደ አንድ ቀን እንዴት ይቆጠራል? ቢባል ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ልማድ ስለሆነ ነው፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ማቴዎስ “ጌታችን ከግብፅ ስደት መልስ ወደ ናዝሬት መጥቶ ኖረ” ብሎ ከጻፈ በኋላ ቀጥሎ በዚያም ወራት መጥምቁ ዮሐንስ፡- መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ ብሎ በይሁዳ ምድረ በዳ እየሰበከ መጣ ብሎ ጽፎአል፡፡ (ማቴ. ፪፥፳፫፤ ፫፥፩) በሁለቱ ዓረፍተ ነገሮች መካከል የሃያ አምስት ዓመታት ልዩነት  አለ፡፡ ብዙውን እንደ አንድ መቁጠር የመጻሕፍት ልማድ ስለሆነ “በዚያ ወራት” ብሎ ጻፈ፡፡ ይህ የትርጓሜ አገባብ የበለጠ ትርጒም የሚሰጥ ነው፡፡ ከማንኛውም መንፈሳዊ  አገልግሎትና ተአምራት በፊት  መጾምና  መጸለይ

እንደሚቀድም ያስተማረንም  ከቃናው  ተአምር በፊት በገዳመ ቆሮንቶስ በመቆየቱ ነው፡፡

የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች

  • ቤተ ዘመድ ናትና ተጠርታ።
  • እመቤታችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሥጋዊ ዕድገቱ እንደምትቀድመው ሲያጠይቅ። እንኳን የእርሱ እናት ትቅርና ዮሐንስ መጥምቁም በ፮ ወር ይቀድመው ነበር፡
  • አስቀድማ የነበረችውንና ከኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን በፊት የኖረችውን ድንግል ማርያምን ሳናውቅ ኢየሱስን እናውቃለን ማለት አይቻልም ሲል፡፡

ወይኑ ባለቀ ጊዜ “ወይን የላቸውም” አለች፡፡

የወይኑን ማለቅ ለእመቤታችን ማን ነገራት? ሙሽራው ወይስ ከሠርገኞቹ መካከል አንዱ? ለዚህ ምንም ዓይነት መልስ እንደማይሰጥ ግልጽ ነው፡፡ ድንግል ማርያም ግን ራሷ ነበር ያወቀችው፤ ነቢይት ናትና፡፡ ስለሆነው እንዲሁም ስለሚሆነው ታውቃለች፤ ቅዱስ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ካመሰገኗት በኋላ “ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብጽዕት ይሉኛል” ማለቷ ወደፊት ስለሚመጣው ትውልድ ነበር የተናገረችው፤ ይህ ነቢይነቷን የሚገልጽ ነው፡፡ (ሉቃ. ፩፥፵፰-፵፱)

ኢሳይያስ በትንቢቱ “ወደ ነቢይቱ ሄድኩ ጸንሳም ነበር” (ኢሳ. ፰፥፩) የሚላት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ነው፡ በሶርያ የነበረው ንጉሥ በኢየሩሳሌም ያለውን ንጉሥ ሊወጋ (ሊገድል) በፈለገ ጊዜ በእልፍኝ ሆኖ የሚመክረውን ምክር ነቢዩ ኤልሳዕ ኢየሩሳሌም ሆኖ ይመለከትና ያውቅ ነበር፤ ኢየሩሳሌም ሆኖ በሶርያ የሚደረገውን እያየ ነበር፡፡ ስለዚህም የኢየሩሳሌሙን ንጉሥ “ከቤትህ እንዳትወጣ ሶርያውያን ሊገድሉህ ይፈልጋሉ” (በ፩ኛ ነገ. ፮፥፰) እያለ ይመክረው ነበር፡፡ ምን ዓይነት ጸጋ እንደሆነ አስቡት፤ ኢየሩሳሌም ሆኖ በሶርያ የሚደረገውን ነገር ማወቅ፡፡ ታዲያ በዘመነ ብሉይ የነበሩ ነቢያት እንዲህ የርቀቱን ነገር የሚያውቁ ከሆነ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የዶኪማስን የቤት ችግር፤ የወይን ማለቅ ብታውቅ ብትረዳ ምን ይደንቅ። የመለኮት እናትም እንዴት ጸጋው ይበዛላት፤ እንደ እመቤታችንስ ጸጋው የበዛለት በዘመነ ብሉይ ማን ነበር። “ጸጋን የተመላሽ ድንግል ሆይ ደስ ይበልሽ” የተባለች ድንግል ማርያም አይደለችምን?

“ከአንቺ ጋር ምን አለኝ”

፩. “ያልሽኝን እንዳልፈጽምልሽ ምን የሚከለክለኝ ነገር አለ” ሲል ነው፡፡ “እናትና አባትህን አክብር፤ ለእናትና ለአባትህ ታዘዝ” ያለ አምላክ እናቱን ሂጂልኝ፤ ወግጅልኝ አላት ሲባል አያሳፍርም? ይህማ እንዳይሆን “ለእናቱ እየታዘዘ አደገ” ወንጌል ይል የለምን፡፡ (ሉቃ. ፪፥፶፩)

፪. ውኃውን ጠጅ አድርግላቸው ብትዪኝ አይሆንም እልሽ ዘንድ ውኃውን ጠጅ ላላደርግላቸው ከሠርግ ቤት ተጠርቼ መጥቻለሁን? ውኃውን ጠጅ ላደርግላቸው ነው።

፫. በአምላክነቱ አገብሮ ተአዝዞ እንደሌለበት ለማጠየቅ

“ጊዜዬ ገና አልደረሰም”

፩. ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ አለውና በቀትር የሚሠራውን በሠለስት አይሠራም፤ በሠለስት የሚሠራውን በነግህ አይሠራምና።

፪. ወይኑ ከእንስራው ፈጽሞ አላለቀም ነበር። ያለውን አበርክቶት ቢሆን ያኑ አበረከተው ተብሎ ተአምራቱ ድንቅ ባልተባለ ነበርና።

፫. ይሁዳ ወጥቶ ነበርና ከተአምራቱ ቢለየኝ ከሞቱ ገባሁበት እንዳይል።

፬. ለዓለም ቤዛ የምሆንበት፣ በመስቀል ላይ የምሰቀልበት ሰዓቱ ገና ነው ሲል ይህን ተናገረ። (ትርጓሜ ወንጌል ዘዮሐንስ ፪፥፬)

የሠርጉ ባለቤት ማን ነበር?

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ሙሽራው ማን እንደሚባል እና ሙሽራዋም ማን እንደሆነች የሚገልጽ የለም። በግብረ ሕማማት ረቡዕ ምሽት ሦስት ሰዓት ምንባብ ላይ በሚገኘው ተዓምረ ኢየሱስ የሙሽራው ስም ዶኪማስ እንደሆነ ይናገራል። ስለ ሙሽራዋ ግን ምንም አይገልጽልም። የተዓምሩ ክፍል እንድህ ይላል፦

“ናትናኤልም ባቲላስ በሚባል አገር ሳለ ይህችውም በገሊላ አውራጃ የምትገኝ የቃና ምድር ናት። በዚያች በቃና ሠርግ በተደረገ ጊዜ ጌታችን ወደ ሠርጉ ግብዣ ይመጣና ይባርካቸው ዘንድ ናትናኤል ለምኖ እንዲያመጣው ዘመዶቹ ማለዱት፤ የሙሽራውም ስሙ ዶኪማስ ይባላል። እርሱም የዮካን ልጅ ነው። ናትናኤልም ወደ ጌታ ኢየሱስ ሂዶ “ጌታችን ሆይ የአባቴ የወንድም ልጅ ወደሆነው ወደ ዶኪማስ ሠርግ ትመጣልን ዘንድ የሠርጉንም ቤት ትባርክ ዘንድ እለምንሃለሁ” አለው። ጌታችን ኢየሱስም ጥሪውን ተቀብሎ አብሮ ወደ ሠርጎ ቤት ሄደ። ወደዚያም በገባ ጊዜ በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ማርያም እና ሰሎሜ ወደ ሠርጉ ይመጡ ዘንድ ሰው ተላከ እነሱም መጡ” ይላል። (ተአምረ ኢየሱስ)

በተአምረ ኢየሱስ አገላለጽ ሙሽራው የሐዋርያው የናትናኤል አጎት የዮካን ልጅ ዶኪማስ ነው። ሌላው ወንጌላዊው የቅድስት ሰሎሜን መገኘት ያልጻፈ ቢሆንም ከድንግል ማርያም ጋር በሠርጉ ቤት ታድማለች። ይህን መሠረት በማድረግ ትርጓሜ ወንጌል የእመቤታችንን በሠርጉ መገኘት “ቤተሰብ ነች” በማለት ይገልጻል። (ትርጓሜ ወንጌል ዘዮሐንስ ፪፥፩)

የቅዱስ ሚካኤል በዓል እንዴት አብሮ ይከበራል?

ቅዱስ ሚካኤል እስራኤል የተባለ ያዕቆብ ከወንድሙ ከኤሳው ጋር ተጣልቶ ፈርቶ ሳለ የረዳው እና ዮርዳኖስን አሻግሮት ወደ እናቱ ወንድም ወደ ላባ ሄደ። ያዕቆብ የአጎቱን ልጆች ልያንና ራሔልን አግብቶ ብዙ ገንዘብ እና ልጆች አፈራ። በኋላም ከንብረቱ እና ከልጆቹ ጋር ቅዱስ ሚካኤል መንገድ እየጠረገና እያቀና ወደ አገሩ በሰላም መለሰው። ወንድሙ ኤሳውም በፍቅር ተቀበለው። ቅዱስ ሚካኤል ለያዕቆብ ዮርዳኖስን ከፍሎ ያሻገረበትን መታሰቢያ “የውኃን በዓል በውኃ” ለማክበር አባቶች ሥርዓት ሠርተው እናከብራለን።

ጥምቀት

የጥምቀት ትርጉም እና ምንነት

ጥምቀት ማለት አጥመቀ(አጠመቀ) ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም መነከር፣ መጥለቅ፣ መደፈቅ፣ በውኃ ውስጥ መጠመቅ ማለት ነው። በሌላ አገላለጽ፡- ጥምቀት አስተርእዮ ወይም መገለጥ  ማለት ነው። (ነገረ ሃይማኖት ዘተዋሕዶ ገጽ ፻፵፭)። በግሪክ ደግሞ ኤጲፋንያ ሲባል ትርጓሜውም መለኮት የተገለጠበት ማለት ነው (ስንክሳር ዘጥር ፲፩)።ይህም የእግዚአብሔር አንድነት እና ሦስትነት የተገለጠበት ታላቅ ምሥጢር መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ እግዚአብሔር የሦስትነቱን ምሥጢር ገልጦበታልና አብ ከሰማይ ሆኖ “የምወደው፣ በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” (ማቴ. ፫፥፲፮-፲፯) እያለ ሲመሰክር ወልድም በዕደ ዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ ሲጠመቅ፣ መንፈስ ቅዱስም በነጭ ርግብ አምሳል በራሱ ላይ ሲቀመጥ ታየ ወይም ተገለጠ። 

ጥምቀት የሰው ልጆች ሁሉ ከአዳም ጀምሮ የወረስነውን ኃጥአት ደምስሶ በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን እንጠራና ዳግም እንድንወለድ የሚያደርገን የመጀመሪያው ምሥጢር የተፈጸመበት ነው። የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከምሥጢራት ሁሉ አስቀድሞ የፈጸመው ታላቅ ምሥጢር ነው። ስለዚህ ከምሥጢራት ሁሉ ጥምቀት ይቀድማል። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን ከመምረጡ በፊት፣ ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ ሄዶ ከመጾምና ከመጸለዩ አስቀድሞ፣ ትምህርት ማስተማር እና ተዓምራት ከማድረጉ በፊት የመጀመሪያ ያደረገው በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ በመጠመቅ ምሥጢረ ጥምቀትን መሠረተ። የመንፈስ ቅዱስ ሱታፌ የሚገኘው በምሥጢረ ጥምቀት ነውና። ሥጋዊ ልደት አንድ እንደሆነ ሁሉ መንፈሳዊ ልደትም አንድ ጊዜ የሚፈጸም ነው። ስለዚህ ጥምቀት አይደገምም። “ጌታ አንድ ነው፣ ሃይማኖትም አንዲት ናት፣ ጥምቀትም አንዲት ናት” (ኤፌ. ፬፥፭)                                                      

ጥምቀተ ክርስቶስ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ መጠመቁን ሲያመለክት “ያን ጊዜ ኢየሱስ በዮሐንስ ሊጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ።” በማለት ወንጌላዊው ማቴዎስ ይነግረናል፡፡ (የማቴ. ፫፥፲፫)

ጌታችንን የሚያጠምቀው መጥምቁ ዮሐንስ እንደሆነ በትንቢትም የተገለጠ ነው። ይህንንም ከዐበይት ነቢያት መካከል ኢሳይያስ “ የአዋጅ ነጋሪ ቃል፦ የእግዚአብሔርን መንገድ ጥረጉ፥ ለአምላካችንም ጐዳና በበረሃ አስተካከሉ።” (ኢሳ. ፵፥፫) ሲል፤ ወንጌላውያንም የትንቢቱን  ፍጻሜ አስተባብረው አረጋግጠውታል። “በነቢዩ በኢሳይያስ፦ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮህ ሰው ድምፅ የተባለለት ይህ ነውና።” (ማቴ. ፫፥፫) በማለት ሲገልጸው፤ “እነሆ፥ መንገድህን የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ፤ የጌታን መንገድ አዘጋጁ፤ ጥርጊያውንም አቅኑ፤ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ ተብሎ በነቢዩ በኢሳይያስ እንደ ተጻፈ፥” (ማር. ፩፥፪-፫)፤ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስም “በነቢዩ በኢሳይያስ ቃል መጽሐፍ፦ የጌታን መንገድ አዘጋጁ ጥርጊያውንም አቅኑ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፤ ዐዘቅቱ ሁሉ ይሙላ ተራራውና ኮረብታውም ሁሉ ዝቅ ይበል፥ ጠማማውም የቀና መንገድ ይሁን፥ ሸካራውም መንገድ ትክክል ይሁን፤ ሥጋም የለበሰ ሁሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ ተብሎ እንደ ተጻፈ ለኃጢአት ስርየት የንስሐን ጥምቀት እየሰበከ በዮርዳኖስ ዙሪያ ወዳለችው አገር ሁሉ መጣ።” (ሉቃ. ፫፥፫-፮)፤ “እርሱም፦ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለ፦ የጌታን መንገድ አቅኑ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ እኔ ነኝ አለ።” (ዮሐ. ፩፥፳፫) በዚህም መሠረት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በ፴ ዘመኑ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ፡፡

ጌታችን ለምን ተጠመቀ?

ጌታችን እንደ አይሁድ የመንጻት ልማድ ከኃጢአት ለመታጠብ አይደለም። እንደ ኃጥአን መጽብሐን ከዮሐንስ ዘንድ ለንስሓ እንደተጠመቁትም ጥምቀት አይደለም። (ዘሌ. ፲፭፥፩-፲፫፤ ማቴ. ፫፥፮) “በይሁዳና በኢየሩሳሌም፣ በዮርዳኖስም ያሉ ሰዎች ወደ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እየመጡ ኃጢአታቸውን እየነገሩት በዮርዳኖስ ያጠምቃቸው ነበር።” ምን እያለ ያጠመቃቸው ነበር? ቢባል “እገሌ ተጠመቅ በማየ ንስሓ ከመ ትኩን ረድኦ ለክርስቶስ፤ እገሌ ለክርስቶስ አገልጋይ ትሆን ዘንድ በንስሓ ውኃ ተጠመቅ” እያለ ያጠምቃቸው ነበር። (ትርጓሜ ወንጌል ዘማቴዎስ)።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ለምን ተጠመቀ?

፩. ለእኛ ሥርዓተ ጥምቀትን ለመመስረት (ዳግም ልደትን ለመስጠት)

፪. ትሕትናን ለማስተማር፦ ዮሐንስን መጥተህ አጥምቀኝ ከማለት ወይም ባሪያ ወደ ጌታው ከመሄድ ጌታ ወደ ባሪያው ሂዶ በባሪያው እጅ መጠመቁ ትሕትናውን ያመለክታልና። ጌታችን ወደ መጥምቁ ዮሐንስ መምጣቱ ለዮሐንስ ክብር ስለሆነው ክብሩን በሚገልጽ አገላለጽ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት ተባለ።

፫. ለአብነት፦ ጌታችን ዮሐንስን መጥተህ አጥምቀኝ ቢለው ነገሥታትና ካህናትን ወደ እኛ መጥታችሁ አጥምቁን እንዳይሉ ሂዳችሁ ተጠመቁ ለማለት አብነት ለመሆን።

፬. ዮርዳኖስን  ብርህት ማኅፀን ለማድረግ (ውኃን ለመባረክ)፦ ለጥምቀት ኃይል ለመስጠት

፭. አንድነቱንና ሦስትነትን ለመግለጥ ጌታችን ተጠመቀ፡፡

ለምን በዮርዳኖስ ተጠመቀ

፩. ትንቢቱን ለመፈጸም፡- “ባሕርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ግብአ ድኅሬሁ፤ ባሕር አየች ሸሸችም ዮርዳኖስም ወደ ኋላ ተመለሰ” (መዝ. ፻፲፫፥፫)

፪. ምሳሌውን አማናዊ ለማድረግ፦ ዮርዳኖስ ከላይ ነቁ አንድ ነው፣ የሰው ሁሉ ነቁ፤ መገኛው አንድ አዳም ነው። ዝቅ ብሎ በደሴት ለሁለት ይከፈላል። እስራኤል በግዝረት፣ አሕዛብ በቁልፈት መለያየታቸውን ያሳያል፤ ወረድ ብሎ ደግሞ ይገናኛል። ይህም ጌታ በጥምቀቱ ሕዝብና አሕዛብን አንድ ሊያደርግ መምጣቱን ያመለክታል።

፫. የዕዳ ደብዳቤያችንን ሊደመስስልን፦ ዲያብሎስ መጋረጃ ጋርዶ በአዳም እና በሔዋን መከራን አጸናባቸው። ስመ ግብርናታችሁን ጽፋችሁ ብትሰጡኝ አቀልላችኋለሁ አላቸው። “አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ፤ ሔዋን አመቱ ለዲያብሎስ” ብለው ጽፈው ሰጡት። መጻፍስ የለም ይሁንብን ማለታቸውን ለመናገር ነው እንጂ እሱ በሁለት ዕብነ ሩካም ጽፎ አንዱን በሲዖል፣ አንዱን በዮርዳኖስ ጥሎታል። በዮርዳኖስ የጣለውን ጌታ ሲጠመቅ እንደ ሰውነቱ ረግጦ፣ እንድ አምላክነቱ አቅልጦ አጥፍቶታል። በሲዖል የጣለውን በዕለተ ዓርብ በአካለ ነፍስ ወርዶ ነፍሳትን ሲያወጣ አጥፍቶላቸዋል።  በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንን በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፤ እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል። (ቆላ. ፪፥፲፬) ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምም “ወሰጠጠ መጽሐፈ ዕዳሆሞ፤ የዕዳ ደብዳቤያቸውን ቀደደ” (ሰኞ ውዳሴ ማርያም)።   ነቢየ እግዚአብሔር  ኤርምያስ ስለ ዕዳ መጽሐፍ ሲናገር “የይሁዳ ኃጢአት በብረት ብርዕ በደንጊያ ሰሌዳ ተጽፎአል።” ይላል (ኤር. ፲፯፥፩)

ለምን በውኃ ተጠመቀ?

. ትንቢቱን ለመፈጸም፡

ሀ. “ጥሩ ውኃንም እረጫባችኋለሁ፤ እናንተም ከርኵሰታችሁ ትነፃላችሁ”  ጥሩ ውኃ የተባለ የጥምቀት ውኃ ነው፡፡ (ሕዝ. ፴፮፥፳፭)

ለ. “አቤቱ ውኖች አዩህ፤ ውሆችም አይተውህ ፈሩ” (መዝ. ፸፮፥፲፮)

ሐ.  “ድሆችና ምስኪኖች ውኃ ይሻሉ”  (ኢሳ. ፵፩፥፲፯)

መ. “ወይቤ ኩሎሙ እለ ጸምዑ ይሑር ኀበ ማይ፤ እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ ወደ ውኃ ኑ” (ኢሳ. ፶፭፥፩)

፪ኛ. ምሳሌው ለመመሰል፡

“ለታውጽእ ባሕር ኮሎ ዘይትሐውስ ዘቦ መንፈሰ ሕይወት” ባለ ጊዜ በልብ የሚሳቡ፣ በእግር የሚሽከረከሩ፣ በደመ ነፍስ ሕያዋን ሁነው የሚኖሩ ፍጥረታት ተገኝተዋል። በረው የሄዱ አሉ፣ የኢጥሙቃን፤ በዚያው የቀሩ የጥሙቃን ምሳሌ ነው። (ዘፍ. ፩፥፳፣ አክሲማሮስ ዘሐሙስ) አንድም በልብ የሚሳቡ የሰብእ ዓለም፣ በእግር የሚሽከረከሩ ከትሩፋት ወደ ትሩፋት የሚሄዱ የባሕታዊያን፣ በክንፍ የሚበሩ ተመስጦ ያላቸው የሰማዕታት ምሳሌ ነው።

፫ኛ. ፍጻሜውና ምሥጢሩ፦

  • ውኃ በዙፋን ካለ ንጉሥ በአደባባይ እስካለ ጽኑስ ለሁሉ ተመሳሳይ ነው። የጥምቀት መሠረቱ ለሁሉ ነውና፣
  • ውኃ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ይፈሳል። ጥምቀትም ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይደረጋልና፣
  • ውኃ ያነጻል፤ ጥምቀትም ያነጻናል።
  • ውኃ የወሰደው ፍለጋ የለውም። በጥምቀት የተሰረየ  ኃጢአት በፍዳ አይመረመርም፣
  • ውኃ መልክ ያሳያል፣ ያለመልማል። ጥምቀትም መልክአ ነፍስ ያሳያልና መልክአ ነፍስ ያለመልማል፡፡

፬ኛ. ውኃ ቀድሞ ሰብአ ትካትን በኋላ ግብፃውያንን አጥፍቶ ስለነበር ለመዓት እንጂ ለምሕረት አልተፈጠረም ብለው ስለነበር ለምሕረትም እንደተፈጠረ ለመጠየቅ ጥምቀቱን በውኃ አድርጓል። (ትርጓሜ ወንጌል፤ ማቴ. ፫፥፲፯)

ለምን በ ፴ ዘመኑ ተጠመቀ?

  • ሰው ሁሉ በ፴ ዘመኑ ሕገ ነፍስን ይሠራል፤ ቅስና እና ምንኩስናም በ፴ ዘመን ይገባል ሲል ነው፡፡(ዘፀ. ፬፥፫፤፩ኛዜና ፳፫፥፬፤ ፩ኛጢሞ. ፫፥፮-፲)
  •  አዳምን የ፴ ዘመን ጎልማሳ አድርጎ ፈጥሮት የሰጠውን ልጅነት አስወስዶ ነበርና የአዳምን ልጅነት ለመመለስ በ፴ ዘመኑ ተጠመቀ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን በማን ስም አጠመቀው?

ጌታችን ዮሐንስን አጥምቀኝ ባለው ጊዜ “ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ አንተን በማን ስም ላጥምቅህ? በአብ ስም እንዳላጠምቅህ አብ አባትህ በአንተ ሕልው ነው፣ በወልድ ስም እንዳላጠምቅህ ወልድ አንተ ነህ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም እንዳላጠምቅህ መንፈስ ቅዱስ ሕይወትህ በአንተ ሕልው ነው፤ ታዲያ በማን ስም ላጥምቅህ?” ብሎ ቢጠይቀው ጌታም ፦ “ወልዱ ለብሩክ ከሳቴ ብርሃን ተሣህለነ፤ አንተ ካህኑ ለዓለም በከመ ሲመቱ ለመልከ ጼዴቅ፤ እንደ መልከ ጼዴቅ ሥርዓት አንተ የዓለም ካህን ብርሃንን የምትገልጥ የአብ የባሕርይ ልጅ ሆይ ይቅር በለን”ብለህ አጥምቀኝ አለው፡፡ (ትርጓሜ ወንጌል ዘማቴ. ፫፥፲፮)

የጥምቀት አስፈላጊነት እና ጥቅም

. ለድኅነት (ለሥርየተ ኃጢአት)

አንድ ሰው መንፈሳዊ ልደትን የሚያገኘው በጥምቀት እና በእምነት ነው። ክርስቲያኖች መንፈሳዊ ልደትን ለመግኘት የግድ መጠመቅ አለባቸው። ያለ ጥምቀት ክርስትና የለም። ጥምቀት አዲስ ሕይወትን የሚያስጥና ክርስቲያናዊ ሕይወትን የሚያስገኝ ነው። ጌታችን  “ያመነ የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል።” (ማር. ፲፮፥፲፮) በማለት ጥምቀት ለመዳን የግድ አስፈላጊ መሆኑን አረጋግጦልናል። ቅዱስ ጳውሎስም ጥምቀት ለመዳን አስፈላጊ መሆኑን ሲገልጽ “እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፥ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለ ነበረው ሥራ አይደለም።” (ቲቶ ፫፥) ይላል።

ቅዱስ ጴጥሮስ ለመዳን አስፈላጊ የሆነውን ጥምቀት ምሳሌውን ተርጉሞ ሲናገር “ ጥቂቶች ማለት ስምንት ነፍስ በውኃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ፥ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኅ ዘመን በዘገየ ጊዜ ቀድሞ ክደውት ለነበሩት ሰበከላቸው፤ አሁንም እኛን በዚያው አምሳል በጥምቀት   ያድነናል፥ ሥጋን በዕድፍ በታመጠብ አይደለም፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ በመነሣቱ በእግዚአብሔርን መልካም ግብርን ያስተምር ዘንድ ነው እንጂ፡፡ (፩ኛጴጥ. ፫፥፳-፳፩) በማለት ጥምቀት የሰውነትን እድፍ ማስወገድ ሳይሆን ውስጣዊ እድፍን (ኃጢአትን) ማስወገጃ ምሥጢር መሆኑን ይመሰክራል።

ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፦ “ንስሓ ግቡ፥ ሁላችሁም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ ኃጢአታችሁም ይሰረይላችኋል፡፡ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ።” (ሐዋ. ፪፥፴፰)  ቅዱስ ጴጥሮስ ያስተማራቸውን አይሁድ የዘለዓለም ሕይወትን እንዲወርሱ ማድረግ ያለባቸውን ሲናገር መጠመቅ እንዳለባቸው አረጋግጧል።

. ለዳግም ልደት

አንድ ሰው በሥጋው ከእናት እና አባቱ እንደሚወለድ ከመንፈስ ቅዱስም በጥምቀት አማካኝነት መንፈሳዊ ልደትን ይወለዳል። “ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።” (ዮሐ. ፫፥፭) በጥምቀት የሚገኘው ልጅነት የማይጠፋ እና ዘለዓለማዊ የልጅነት ማረጋገጫ ነው። “ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም፥ በሕያውና ለዘለዓለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ።” (፩ኛ የጴጥ. ፩፥፳፫)

በጥምቀት የምናገኘው የልጅነት ጸጋ የመንግሥቱ ወራሾች ያደርገናል።ልጆችም ስለ ሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮኽ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ። ለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ።” (ገላ. ፬፥፮-፯) ጥምቀት ከዲያብሎስ ባርነት ወጥተን የእግዚአብሔርን ልጅነት የምናገኝበት፣ የመንግሥቱ ወርሽ የምንሆንበት ምሥጢር ነው።

. ከክርስቶስ ጋር አንድ መሆን

ጥምቀት የጌታችንን ሞቱን እና ትንሣኤውን ማመናችንን በተግባር የምንመሰክርበት እና ከሞቱ እና ከትንሣኤው የምንሳተፍበት ምሥጢር ነው።  ስንጠመቅ ወደ ውኃ ውስጥ መግባታችን የሞቱና የመቀበሩ ምሳሌ ነው። መውጣታችን ደግሞ የመነሣቱ ምሳሌ ነው። “ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ የተጠመቅን ሁላችን ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ እንደ ተጠመቅን አታውቁምን? እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፥ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን። ሞቱንም በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን።” እንዲል (ሮሜ ፮፥ ፫)   

ከውኃ ውስጥ ሦስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ ማለቱ ጌታ በመቃብር ውስጥ ሦስት ቀን እና ሌሊት መቆየቱን ያስረዳል። በሦስተኛው ከውኃ መውጣቱ ጌታ በሦስተኛው ቀን ከመቃብር ለመውጣቱ ማስረጃ ነው። ክርስቲያኖች ከክርስቶስ ጋር እንነሣለን። በመጀመሪያ የነፍስ ትንሣኤን እናገኛለን። በመጨረሻ ደግሞ ነፍስና ሥጋቸን ተዋሕደው እንነሣለን። የነፍስ ትንሣኤ የተባለው በእምነትና በጥምቀት የምናገኘው ትንሣኤ ሲሆን በነፍስ ገነት መግባትን ያመለክታል። (ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት ገጽ ፪፻፵፯)።

. ክርስቶስን ለመልበስ

አሮጌውን አዳማዊ ሰውነታችንን አስወግደን “አዲስ ሰው” የተባለ ዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስን የምንለብሰው በጥምቀት ነው። ጥምቀት ለሕይወት የሆነ አዲስ ሰውነትን ገንዘብ የምናደርግበት ምሥጢር ነው። “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና።” (ገላ. ፫፥፳፯) ያልተጠመቀ ሰው ማንም ቢሆን ክርስቶስን ሊለብስ እና አዲስ ተፈጥሮን ገንዘብ ማድረግ አይችልም። “እርስ በርሳችሁ ውሸት አትነጋገሩ፥ አሮጌውን ሰው ከሥራው ጋር ገፋችሁታልና። የፈጠረውንም ምሳሌ እንዲመስል ዕውቀትን ለማግኘት የሚታደሰውን አዲሱን ሰው ለብሳችሁታል።” (ቆላ. ፫፥፱-፲)

. መንግ ሰማያትን ለመውረስ

ጥምቀት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርስበት ነው። እግዚአብሔር የሰጠንን ጸጋ ለመቀበል በጥምቀት የእግዚአብሔር ልጆች ሆነን ካልተወለድን በስተቀር ከእናት ከአባት በተወለድነው ተፈጥሯዊና ሥጋዊ ልደት መንፈሳዊ እና ሰማያዊ የሆነውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ አንችልም። “ኢየሱስም መልሶ፦ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም” (ዮሐ. ፫፥፭) አለው።  ጥምቀት አዲስ ልደት ተብሏል። “እንደ ምሕረቱ መጠን ለአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብና በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ አዳነን እንጂ፥ እኛ ስላደረግነው በጽድቅ ስለ ነበረው ሥራ አይደለም” (ቲቶ ፫፥፭)

. የቤተ ክርስቲያን አባል ለመሆን

በኦሪተ የተገረዙ ሁሉ የእግዚአብሔር ወገንነትን መብት እንደሚያገኝ ሁሉ በጥምቀት የቤተ ክርስቲያን አባልነት መብት እናገኛለን። ምክኛቱም ግዝረት በጥምቀት ተተክቷልና።

“የሥጋንም ሰውነት በመገፈፍ፥ በክርስቶስ መገረዝ፥ በእጅ ባልተደረገ መገረዝ በእርሱ ሆናችሁ ደግሞ ተገረዛችሁ፤ በጥምቀትም ከእርሱ ጋር ተቀብራችሁ፥ በጥምቀት ደግሞ፥ ከሙታን ባስነሣው በእግዚአብሔር አሠራር በማመናችሁ፥ ከእርሱ ጋር ተነሣችሁ። እናንተም በበደላችሁና ሥጋችሁን ባለመገረዝ ሙታን በሆናችሁ ጊዜ፥ ከእርሱ ጋር ሕይወትን ሰጣችሁ፤ በደላችሁን ሁሉ ይቅር አላችሁ፤ በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፤ እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል።” (ቆላ. ፫፥፲፩-፲፫)

የጥምቀት ምሳሌ በብሉይ ኪዳን

፩. አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ ከመልከ ጼዴቅ ጋር መገናኘቱ፦ አበ ብዙኃን አብርሃም ለአምስቱ ነገሥተ ሰዶም ረድቶ አራቱን ኮሎዶጎሞርን ድል ነሥቶ ሲመለስ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ሲሔድ መልከ ጼዴቅ ኅብስተ በረከት ጽዋዓ አኮቴት ይዞ ተቀብሎታል። አብርሃም፦ የምእመናን፣ ዮርዳኖስ፦ የጥምቀት፣ መልከ ጼዴቅ፦ የቀሳውስት፣ ኅብስተ በረከት ጽዋ አኮቴት፦ የሥጋው የደሙ ምሳሌ ነው።

፪ ኢዮብ ከዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ ከደዌው ድኗል። ኢዮብ፦ የአዳም፣ ደዌ፦ የመርገመ ሥጋ የመርገመ ነፍስ፣ ዮርዳኖስ ፦ የጥምቀት ምሳሌ ነው።

፫. እስራኤል ዮርዳኖስን ተሻግረው ምድረ ርስት እንደገቡትም እመናንም አምነው ተጠምቀው ገነት መንግሥተ ሰማያት ለመግባታችን ምሳሌ ነው።

፬. ንዕማን በዮርዳኖስ ተጠምቆ ከደዌው ተፈውሷል። ንዕማን፦ የአዳም፣ ደዌ፦ የመርገመ ሥጋ፣ የመርገመ ነፍስ፣ ዮርዳኖስ፦ የጥምቀት ምሳሌ ነው።

የጥምቀት ዓይነቶች

ጥምቀት ከሦስት ወገን ነው።

፩ኛ. መዝገበ ውሉድ ፍቁራን የምትባል የጌታ ጥምቀት

፪ኛ. ጥምቀተ ዮሐንስ

፫ኛ. ጥምቀተ አይሁድ ናቸው።

ጥምቀተ አይሁድ እና ጥምቀተ ዮሐንስ አንድ አይሆንም ሁሉም ልጅነት አያሰጥም ቢሉ አንድ አይደሉም፤ ከሰውነታቸው ሰውነቱ እንዲበልጥ ከጥምቀታቸውም ጥምቀቱ ይበልጣል። አንድም ጥምቀት ከስምንት ወገን ነው። አራቱ ምሳሌያዊ አራቱ አማናዊ ናቸው።

ምሳሌያዊ የሚባሉት

፩ኛ. አጥመቃ ለምድር በማየ አይህ፤ ምድር በማየ ዐይህ መጠመቅ

፪ኛ. ወለኩሎሙ አበዊነ አጥመቆሙ ሙሴ በደመና፤  “ወንድሞች ሆይ፥ ይህን ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ። አባቶቻችን ሁሉ ከደመና በታች ነበሩ ሁሉም በባሕር መካከል ተሻገሩ፤ ሁሉም ሙሴን ይተባበሩ ዘንድ በደመናና በባሕር ተጠመቁ።” (፩ኛቆሮ. ፲፥፩-፪)

፫ኛ. ወተጠምቃ እገሪሆሙ ለካህናት፤ የካህናት እግሮቻቸው የዮርዳኖስን ውኃ በመርገጣቸው እንደ ጥምቀት ሆናቸው። (ኢያ. ፫፥፲፮)

፬ኛ. ጥምቀት ዮሐንስ፦ ዮሐንስ መጥምቁ ሲያጠምቃት የነበረችው ጥምቀት ናት። ዮሐንስ ለንስሓ በውኃ ብቻ እንጂ በመንፈስ ቅዱስ ስላላጠመቀ የዮሐንስ ጥምቀት የንስሓ እንጂ አማናዊ አልነበረችም።

 አማናዊ ጥምቀት

፩ኛ. መዝገበ ውሉድ ምቁራን የምትባል የጌታ ጥምቀት፦ በ፵ በ፹ ቀን ከውኃ እና ከመንፈስ የምንወለድባት አማናዊቷ ጥምቀት ነች።

. አንብዓ ንስሓ፦ ማለት በንስሓ ጊዜ የሚፈሰው የለቅሶ፣ የሐዘን ዕንባ ነው። የንስሓ ዕንባ ሥርየተ ኃጢአትን ስለሚያሰጥ እንደ ጥምቀት ይቆጠራል። (ድርሳነ ጎርጎርዮስ ፴፱፥፲)

. ደመ ሰማዕት፦ ደምን በማፍሰስ የምትፈጸም ጥምቀት ናት። ይህች ጥምቀት ክርስቶስን መምሰል የምታሰጥ እጅግ የከበረች ጥምቀት ናት፤ ዋጋዋም ከፍ ያለ ነው።

4. ባሕረ እሳት፡- እንደ ደመ ሰማዕታት በእሳት ባሕር ተጠምቆ ድኅነትን መግኘት ነው።

ጥምቀት ስንት ጊዜ ትፈጸማለች?

በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ የምትፈጸም ጥምቀት አንዲት ናት ። አንድ ጊዜ ከተፈጸመች  (ከተሰጠች) አትደገምም። ከቤተ ክርስቲያን የማይደገሙ ምሥጢራት መካከል አንዷ ነች። በካህን፣ በኢጲስ ቆጶስ እጅ የምትፈጸም ጥምቀት አንዲት ነች ። “ሊቀ ጳጳስ ወይም ኢጲስ ቆጶስ ሳይመጣ አናጠምቅም አይበሉ፤ የማጥመቅ ሥልጣን ያለው ያጥምቅ እንጂ፣ የጥምቀት ሥልጣን አንዲት ናት ።” (ፍትሃ ነገሥት አንቀጽ ፫፥፳፱)። አማናዊቱ ጥምቀት አንዲት ናት ። “አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖት፣ አንዲት ጥምቀት።” (ኤፌ. ፬፥፭)

ለምን በየዓመቱ ይከበራል?

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የጥምቀት በዓልን የምታከበረው የጌታችን የማዳኑን ምሥጢር ለማዘከርና  ለመመስከርም ነው፡፡ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ “የጠበሉን መረጨት አይተው  በቀድሞ ዘመን ወደ ሀገራችን መጥተው የነበሩ ኢየሱሳውያን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን  በየዓመቱ ታጠምቃለች” ያሉትን መልስ ሲሰጡ “ይህን ምትፈጽመው ጌታችን ለእኛ ብሎ ያሳየውን ትሕትና ለመመስከር እና  ለምእመናን የጌታችን በረከተ ጥምቀት ለማሳተፍ እንጂ የተጠመቁትን ምእመናን  እየመለሰች በየዓመቱ አታጠምቅም” ብለዋል፡፡(የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ገጽ ፻፳፫)። ስለዚህ የጥምቀትን በዓል በየዓመቱ የምናከብረው ጌታችን ለኛ ያደረገውን የድኅነት መንገድ ለማሰብ፣ ከዲያብሎስ ቁራኝነት ነጻ የወጣንበትን ምሥጢር ለመዘከር፣ ጌታችን ከገሊላ ወደ ዮሐንስ ያደረገውን ጉዞ ለማሰብ፣ ከበዓለ ጥምቀቱ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን ለማግኘት ነው።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር