“ዳግመኛ ልትወለዱ ይገባችኋል” (ዮሐ. ፫፥፯)

ይህንን ቃል የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአይሁድ መምህር ለሆነው ኒቆዲሞስ በጥምቀት ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊወርስ እንደማይችል ባስረዳበት ትምህርቱ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ምንም እንኳን የአይሁድ መምህር ቢሆንም ምሥጢሩን እያመሠጠረ የኦሪትን ትምህርት ቢያስተምርም ስለ ዳግም መወለድ ምሥጢር ተሠውሮበት ጌታችንን ተደጋጋሚ ጥያቄዎችን ሲጠይቅ እንመለከታለን፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ለሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ሲመላለስ ኢአማንያንን በትምህርቱ ፣ የታመሙትን በተአምራት እየፈወሰ፣ አምስት እንጀራና ሁለት አሣን አበርክቶ የተራቡትን አጥግቦ፣ የተጠሙትን አጠጥቶ እንደመሻታቸው ፈጽሞላቸዋል፡፡ ነገር ግን አምላክ ሲሆን የአዳምን ሥጋ ለብሷልና ራሱን “የእግዚአብሔር ልጅ” እያለ ይጠራል በማለት አይሁድ በምቀኝነት ተነሥተው በየጊዜው ይፈትኑት ነበር፡፡ በአንድ በኩል ከሮማውያን ቅኝ ግዛት ነጻ የሚያወጣቸው መሲሕ ይፈልጋሉ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለብዙ ዘመናት በሮማውያን በባርነት ቀንበር ስለ ተሰቃዩ ተስፋ ቆርጠው ነበር፡፡ መሲሕ ቢመጣ እንኳ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት ጦር ይዞ፣ ሠራዊት አስከትሎ እንደሆነ ነበር የሚያምኑት፡፡ ለዚህም ነው የክርስቶስን መሲሕነት ያልተቀበሉት፡፡

ለዚህም ትልቅ ማሳያ የሚሆነን ከፈሪሳውያን ወገን የሆነው የኦሪት መምህሩ ኒቆዲሞስ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን ሰው ለማሰብ የዐቢይን ጾም ሰባተኛ ሳምንት እሑድ በስሙ ሰይማ ታከብረዋለች፡፡ ተከታዮቿ ምእመናንም የእርሱን አሠረ ፍኖት እንዲከተሉ ትመክራለች፤ ታስተምራለችም፡፡

ኒቆዲሞስ ማነው?

ከአይሁድ መካከል ፈሪሳውያን ሕግን የሚያጠብቁ ቀሚሳቸውንም የሚያስረዝሙ፣   የማይፈጽሙትን ሕግ በሕዝብ ላይ የሚጭኑና ራሳቸውን ከሌሎች በላይ ከፍ የሚያደርጉ፣ የአብርሃምን ሥራ ሳይሠሩ አባታችን አብርሃም ነው እያሉ የሚመጻደቁ ናቸው፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ምንም እንኳ ፈሪሳዊ ቢሆንም አለቃ እንዲሆን በሮማውያን የተሾመ ባለ ሥልጣን ነው፡፡

ኒቆዲሞስ ለአይሁድ መምህራቸው ሲሆን የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርቱን ሰምቶ፣ ተአምራቱን አይቶ በፍጹም ልቡ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብሎ የተሠወረውን ይገልጥለት ዘንድ ለመማር ራሱን ከዚህ ሕዝብ ለይቶ በፍጹም ልቡ ክርስቶስን ፍለጋ የመጣ ፈሪሳዊ ነው፡፡ በቀን በብርሃን ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርቦ ለመማር የአይሁድን ክፋትና ተንኮልን ያውቃልና ይህንን ፍራቻ በጨለማ አምላኩን ፍለጋ መጥቷል፡፡ “መምህር ሆይ ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን” በማለትም መስክሯል፡፡ (ዮሐ. ፫፥፪)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የኒቆዲሞስን ምስክርነት ሲሰማም “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” በማለት መልሶለታል፡፡ ኒቆዲሞስ ምሥጢሩ ቢረቅበትና መረዳት ቢሣነው “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይችላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” ሲል ጠይቋል፡፡ ጌታችንም የኒቆዲሞስን ጥያቄ “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፤ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነውና ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ ልትወለዱ ይገባችኋል ስላልሁህ አታድንቅ” በማለት ለእግዚአብሔር ምንም የሚሣነው ነገር እንደሌለና የኒቆዲሞስ አመጣጥ ከልብ መሆኑን አውቆ ምሥጢረ ጥምቀትን (ዳግም ልደትን) ገለጸለት፡፡ (ዮሐ.፫፥፭-፯)

ኒቆዲሞስ ከጌታችን ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር ሥር ጭ ብሎ ተምሯልና በቀራንዮ አደባባይ ራሱን ለዓለሙ ቤዛ አድርጎ ሲሰጥ “እስከ ሞት ከአንተ አንለይህም” ያሉት ደቀ መዛሙርቱ ከዮሐንስ በቀር ሲበታተኑ፣ ቀራንዮ ላይ የተገኘው ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ ጌታችን “ሁሉ ተፈጸመ” ብሎ ነፍሱን ከሥጋው ሲለይ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ሆነው የክርስቶስን  ሥጋ ከአለቆች ለምነው በመገነዝ በአዲስ መቃብር ለመቅበር በቃ፡፡ በዚህ ምክንያት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የዐቢይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት “ኒቆዲሞስ” በማለት ታከብራለች፡፡(ማቴ.፳፮፥፴፩-፴፭፤ ዮሐ. ፲፱፥፴)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

“ለሦስት ቀናት በጾምና በጸሎት በአንድ ልብ ሆነን ወደ ፈጣሪያችንን እንድንጮህ አደራ እንላለን”-ቋሚ ሲኖዶስ

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ የጾምና የምሕላ አዋጅ አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ
የነነዌም ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ ለጾም አዋጅ ነገሩ!
ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ” (ትንቢተ ዮናስ ምዕራፍ 3 ቁጥር 5)
ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በተከሰተው ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ መዋቅሮቿን በመጣስ መፈንቅለ ሲኖዶስ በማድረግ በሕገወጥ መንገድ ኤጲስ ቆጶስነት ሢመት በሰጡትና በተሾመ ግለሰቦች ላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ጥር 18 ቀን 2015ዓ.ም. ቃለ ውግዘት ማስተላለፉ ይታወቃል።
     ይሁን እንጂ እነዚህ ሕገወጥ ቡድኖች ከድርጊታቸው ሊታቀቡ ካለመቻላቸውም በላይ በመንግሥት ኃይሎች በመታገዝ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምታስተዳድራቸውን መንበረ ጵጵስናዎችንና ቢሮዎችን በኃይል በመውረርና በመስበር ከፍተኛ ጥፋት እያደረጉ ከመሆኑም በላይ የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችን ሠራተኞች ካህናትና ምእመናን በማሰርና በማንገላታት ላይ ይገኛል፡፡
መንግሥትም ሕግ ከማስከበር ይልቅ ለሕገ ወጥ ቡድኖች ድጋፍ በመስጠት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕግና መብት ሊያስከብር ስላልቻለ ሁሉን ማድረግ ወደሚቻለው አምላካችን በመማፀን ጸሎትና ምሕላ ማድረጉ አስፈላጊ መሆኑን ቅዱስ ሲኖዶስ ተረድቷል።በመሆነም ጾመ ነነዌን ምክንያት በማድረግ በመላው ዓለም የሚገኙ ሕዝበ ክርስቲያን ጥቁር ልብስ ብቻ በመልበስ በጾምና በጸሎት ምሕላ በመያዝ በቤተ ክርስቲያን ዓውደ ምሕረት በመገኘት ወደ እግዚአብሔር ጾም፤ ጸሎትና ምሕላ እንድታቀርቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
ጥቁር ልብስ የምንለብሰው በመከራ መጽናት ለመግለጽ ነው፡፡
እንደሚታወቀው ጥቁር የእውቀት ምልክት ነው ተማሪዎች አውቀናል ሲሉ ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፡፡ እኛ ከእውቀት በላይ የሆነውን አምላካችንን በመማፀን ከዚህም ማንም ሊያናውጽን እንደማይችል የምናረጋግጥበት፤ ጥቁር የእውነት ምልከት ነው ዳኞች እውነት እንፈርዳለን ሲሉ ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፡፡ እኛም መከራው የሚያሰቅቀን ሳይሆን ይበልጥ ልንጸናና ልንበረታ የሚገባ መሆኑን ለዓለም ሕዝብ የምናሳይበት በመሆኑ ከጥር 29 እስከ የካቲት 1 ቀን 2015 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በጾምና በጸሎት በአንድ ልብ ሆነን ወደ ፈጣሪያችንን እንድንጮህ አደራ እንላለን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በደረሰባት የውስጥ ፈተና ሀዘኗ ከባድ ነው።” ብፁዕ አቡነ አብርሃም

ብፁዕ አቡነ አብርሃም

ብፁዕ አቡነ አብርሃም

        ብፁዕ አቡነ አብርሃም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ይህን የገለጹት ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጪ የተፈጸመውን “የጳጳስ ሹመት” አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ነው።
         ብፁዕነታቸው እንደገለጹት በፈተና የሚያጸናው ሁል ጊዜ ፈተናዎችን እያሳለፈ ለዘመናት ሲጠብቃት የነበረ እግዚአብሔር ዛሬም ጥበቃውና መግቦቱ እንደማይለያት ሙሉ እምነት አለን። በደረሰው ክስተትም እጅግ አዝነናል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ታዝናለች።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከ3ሺ ዘመን በላይ የራሷን አንድነት ከማስጠበቅ አልፋ የሀገርን አንድነት ስታስጠብቅ ለሰው ልጆች አንድነት ትልቁን ድርሻ በመውሰድ ስትሠራ የኖረች አሁንም ያለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነች በማለት ገልጸዋል።
              ይህንን አንድነቷን የሚንድ ሕጋዊ ሰውነቷን የሚጥስ አላስፈላጊ ክስተት ተፈፅሟል። በዚህም ቅዱስ ፓትርያርኩ በአስተላለፉት ጥሪ መሠረት ከሀገር ውስጥ ከሀገር ውጭ የምትገኙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከነገው ዕለት ጀምሮ የቅዱስነታቸውን ጥሪ በመቀበል እንድትገኙ በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል።
ብፁዕነታቸው አክለውም የተፈጠረውን ችግር በዝርዝርና በጥናት ቅዱስ ሲኖዶስ አይቶ የመጨረሻውን ውሳኔ እስከሚሰጥበት ጊዜ ድረስ ምእመናንና አገልጋዮች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሁላችሁም በየአላችሁበት ቤተ ክርስቲያንን እንድትጠብቁ ሲሉ አሳስበዋል። ተመሳስለውና የሌለ ሀሳብ እያቀረቡ ሕዝብን ከሚለያዩ ሠዎች እንድትጠበቁና እንድትጠብቁ በጽናት፣ በትእግስትና በፍቅር ሕጋዊ በሆነ ነገር ሁሉ ቤተ ክርስቲያንን እንድትጠብቋት በአንድነቷ የተረከብናትን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በአንድነቷ ለነገው ትውልድ ለማስረከብ የእያንዳንዳችንን ድርሻ እንድንወጣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ብለዋል።
            በመጨረሻም ሕጋዊ ሰውነቷ የተረጋገጠ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በሕጋዊ ሰውነቷ የመጠበቅ የማስጠበቅ ኃላፊነቱ የመንግሥት ስለሆነ ይህን የተፈጸመውን ግፍ መንግሥት ተመልክቶ የቤተ ክርስቲያኗን ሉዓላዊነት በመጠበቅና በማስጠበቅ የራሱን ድርሻ እንዲወጣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪ አቅርበዋል ።

የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና እና የምክክር መርሐ ግር ተካሄደ

በማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ አዘጋጅነት ለማእከላት ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ዋና ክፍል ኃላፊዎች፣ ለመደበኛ አስተባባሪዎች እና በዋናው ማእከል ለግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባሪያ አባላት የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና እና የምክክር መርሐ ግብር ከኅዳር ፫-፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ተካሄደ፡፡

በማኅበሩ መሰብሰቢያ አዳራሽ ለሁለት ቀናት በተካሄደው ሥልጠናም አዲሱን የማኅበሩን ተቋማዊ ለውጥ በተመለከተ በመጋቤ ሀብታት ታደሰ አሰፋ እና አቶ ግዛቸው ሲሳይ ለአንድ ቀን የቆየ የግንዛቤ ማስጨበጫ የዳሰሳ ጥናት ቀርቧል፡፡ በዚህም የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር ውጫዊና ውስጣዊ ከባቢያዊ ሁኔታን መሠረት አድርጎ አሁን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ በማጤን ተቋማዊ ለውጡ እንደተዘጋጀ ተገልጿል፡፡ የማኅበሩ ለውጥ ከየት ወደ የት ትንተና የቀረበ ሲሆን አዲሱ የማኅበሩ ርእይ፣ ተልእኮ፣ ዕሴት እና ዓላማም በተመለከተ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡

በቀረበው ገለጻ መነሻነትም ከተሳታፊዎች የተለያዩ ጥያቄዎች ቀርበው ምላሽ የተሰጣቸው ሲሆን፤ የቡድን ውይይት፣ እንዲሁም ከአገልግሎት ጋር ተያይዞ የልምድ ልውውጥ እና የምክክር መርሐ ግብር ተካሂዷል፡፡

እሑድ በነበረው መርሐ ግብርም “ውጤታማ መሪነት እና የመሪነት ችሎታ፤ Effective leadership & leadership skill” በሚል ርእስ በመጋቤ ሀብታት ታደሰ አሰፋ እንዲሁም “ተግባቦት፤ Communication” በሚል ርእስ በዶ/ር ወርቁ ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ በተሰጡት ሥልጠናዎች ላይ ከተሳታፊዎች ጥያቄዎች ቀርበው በጥናት አቅራቢዎቹ ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

በሥልጠናው ላይ ተሳታፊዎች ከነበሩት አባላት መካከል ቆይታቸውን በተመለከተ ሲገልጹ “ከአቀባበሉ ጀምሮ እስከ ፍጻሜው መልካም ጊዜን አሳልፈናል፡፡ ተቋማዊ ለውጡ ላይ ያለንን ብዥታ ያጠራንበት፣ በሌሎቹም በተሰጡን ሥልጠናዎች በቂ ዕውቀት መጨበጥ ችለናል፡፡ በተለይም ያካሄድናቸው የልምድ ልውውጦች ለአገልግሎት እንድሣሣ እና እንድንበረታ የሚያደርጉን ናቸው” በማለት ገልጸዋል፡፡

በዚህ መርሐ ግብር ከ፴፩ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት የተውጣጡ ፵፫ ተሳታፊዎች የተካፍለዋል፡፡

ቁስቋም ማርያም

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጋር ወደ ግብፅ እንደሚሰደድ ወይወርድ እግዚእነ ውስተ ምድረ ግብፅ እንዘ ይጼዐን ዲበ ደመና ቀሊል፤ ጌታችን በፈጣን ደመና (በእመቤታችን ጀርባ) ተጭኖ ወደ ግብፅ ይወርዳል ብሎ በተናገረው ትንቢት መሠረት ስደትን ለመባረክ፣ የግብጽን ጣኦታት ያጠፋ ዘንድ ተሰዷል፡፡ (ኢሳ. ፲፱፥፩)

ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስም የጌታችንን ስደት በተመለከተ “የእግዚአብሔር መልአክ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ “ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይሻዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱንም ይዘህ ወደ ምድረ ግብፅ ሽሽ፤ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ኑር” በማለት እንደ ጻፈው ቅዱስ ዮሴፍ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ከልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንዲሁም ሰሎሜን ይዞ ወደ ግብፅ ተሰዷል፡፡ (ማቴ. ፪፥፲፫)

ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደ ግብፅ ይሰደዱ ዘንድ እንደነገራቸው ሁሉ ፵፪ ወራት (ሦስት ዓመት ከስድስት ወራት) ሲፈጸም የሄሮድስ መሞት እና ወደ ኢየሩሳሌም ይመለሱ ዘንድ የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሞተዋልና፥ ተነሥተህ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ በማለት ነግሯቸዋል፡፡ (ማቴ.፪፥፲፱-፳፩) በዚህም መሠረት ኅዳር ፮ ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተመለሱበትን ቀን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

ደብረ ቁስቋም በደቡብ ግብፅ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ወደ ግብፅ ከተሰደደች በኋላ አሳዳጅ የነበረው ሄሮድስ በመሞቱ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከስደት ሲመለሱ ያረፉበት ቦታ ነው፡፡ ይህ ቁስቋም ተራራ ጌታችን ብዙ ተዓምራት የፈጸመበት በመሆኑ ተባርኳል፤ ተቀድሷልም፡፡ ይህ ተራራ የተቀደሰ ስለመሆኑ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ታኦፊሎጎስ በድርሳነ ማርያም እንዲህ ብሏል፤ ይህም ከሀገሮቹ ሁሉ ተራሮች የሚበልጥ (የተለየ) ከፍ ያለ ተራራ ነው፡፡ በውስጡ ቅዱስ አግዚአብሔር ያድራል፡፡ ይህንን ተራራ የእግዚአብሔር ልጅ ወዶታል፤ አክብሮታልምና፤ ከዓለም ሀገሮች ሁሉ ከተቀደሰች እናቱ ጋር አድሮባታልና፡፡ ከመላእክት ቤት ያድር ዘንድ አልወደደም፤ ቢታንያንም አልመረጠም፤ ከተራራው ላይ ባለች ገዳም ቤት ውስጥ አደረ እንጂ፤ ነቢዩ ዳዊት፤ የጽዮንን ተራራ ወደደ፤ በአርያምም መቅደሱን ሠራ” እንዳለ፡፡

ሊቁም በመቀጠል ሙገሳውን እንዲህ ሲል ገልጿል፤ አንተ ተራራ ሆይ የእግዚአብሔር ማደሪያ በሆንህ ጊዜ በኪሩቤልና በሱራፌል መካከል ፍጹም ደስታ ተደረገ፡፡ የመላእክት ሠራዊት ቅዱስ የሆነ ፈጣሪያቸውንና ጌታቸውን ይታዘዙ (ያገለግሉ) ነበር፡፡ አንተ ተራራ ሆይ ያደረብህ ጌታችን ስለሆነ ከተራሮች ሁሉ ከደብረ ሲናም ይልቅ ከፍ ከፍ አልህ፤ ጌታችን በደብረ ሲና ባረፈ ጊዜ ፍጹም ደስታ፣ ታላቅ ብርሃንም በሆነ ጊዜ መቅረብና መመልከት ከሙሴ በቀር የቻለ የለም፡፡ እርሱም ቢሆን ፊቱን ማየት አልቻለም፡፡ ሥጋ ለባሽ ሁሉ እርሱን ዐይቶ በሕይወት መኖር የሚቻለው የለምና፡፡ እኛ ግን አየን፤ ከዚህ ማደሩንም ተረዳን፤ ዳግመኛም ንጽሕት በሆነች በማርያም ዘንድ አየነው፡፡ ቅድስት ከሆነች ከእመቤታችን ማርያም ዘንድ በቤተልሔም ስለ እኛ በተዋሐደው ሥጋ በጨለማና በሞት ጥላ ሥር ያለን እኛን ከቸርነቱና ሰውን ከመውደዱ የተነሣ መጥቶ አዳነን፤ ከዓለም ሁሉ ይልቅ ጣዖትን በማምለክ ሲበድሉም ወደ ግብፅ  ሀገር ወርዶ በእነርሱ ላይ የመለኮትነት ብርሃኑን በማብራት ታላቅ የሆነ ክብሩን ገለጠ፡፡” እመቤታችን ቅድስት ማርያምም ከጌታችን ኢየሱስ ጋር በዚህም ተራራ ስድስት ወራት ዐርፈዋል፡፡ (ድርሳነ ማርያም)

ኅዳር ፮ ቀን የሚነበበው የመጽሐፈ ስንክሳር ክፍል ጌታችን ኢየሱስ ዳግመኛም በኋላ ዘመን ሐዋርያትን በደብረ ቁስቋም ሰብስቦ፤ ታቦትንና ቤተ ክርስቲያኑን አክብሮ የቊርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እንደ ሰጣቸው፤ ጌታችንም ካረገ ከብዙ ዘመናት በኋላ በኅዳር ፮ ቀን አስተጋብኦሙ እግዚእነ ለሐዋርያቲሁ ቅዱሳን ውስተ ዝንቱ ደብረ ቊስቋም ወቀደሰ ታቦተ ወቤተ ክርስቲያን ወሠርዐ ቊርባነ ወመጠዎሙ ሥጋሁ ቅዱሰ ወደሞ ክቡረ፤ በዚህ በደብረ ቊስቋም ቅዱሳን ሐዋርያቱን ሰበሰባቸው፤ ታቦትንና ቤተ ክርስቲያንንም አክብሮ የቊርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ሰጥቷቸዋልይላል፡፡ (ስንክሳር ኅዳር ፮)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ንስሓ አባቶችና የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት

ዲ/ን ኢያሱ መስፍን

የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ወጣቱን ወደ መንፈሳዊ ልዕልና ለማድረስ የሚደረግ ውጣ ውረድ የበዛበት ጉዞ ነው። ለዚህም የጉዞው ተሳታፊዎች እና ጉዞውን የተቃና ለማድረግ ከፊት የሚቀድሙ መሪዎች የአገልግሎት ተነሳሽነትና ቁርጠኝነት ለውጤቱ ማማር ትልቁን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡

በየጊዜው የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎት የሚረከቡ ወጣቶች በሚኖራቸው ዕውቀት፣ መረዳት እና ትጋት ልክ አገልግሎቱን ለማስኬድ እንዲሁም ከታለመለት ግብ ለማድረስ መጣራቸው አያጠራጥርም። እነዚህ ወጣቶች ዕቅዶቻቸውን ለማስፈጸም ከሚደረግላቸው መዋቅራዊ ድጋፍ ባለፈ ጽኑ የሆነ መንፈሳዊ እገዛ ያስፈልጋቸዋል። ይህንን እገዛ ደግሞ መስጠት የሚችሉት የንስሓ አባቶች ናቸው

ወደ አንድ ተራራ የሚወጣ ሰው መውጫ መንገዱን በሚገባ የሚያውቅ መሪ ማግኘት ግድ ይለዋል። የንስሓ አባቶችም ድርሻ ይህን የመሪነት እና የመንገድ ጠቋሚነት ሚና መጫወት ነው፡፡ ከዚህ ማስተዋል እንደሚቻለው በንስሓ አባትነት የሚሾሙ ካህናት ኑዛዜ ተቀብለው የኃጢአት ሥርየትን ከማሰጠት ባለፈ የመንፈስ ልጆቻቸውን በምግባር እና በሃይማኖት ወደ ድኅነት ጎዳና የመምራት ሥራን ይሠራሉ።

ማንኛውም መንፈሳዊ ሥራ በዕውቀትና በችሎታ ላይ በተመሠረተ የራስ መተማመን መነሻነት ብቻ ሊከወን አይችልም፡፡ “እግዚአብሔር ቢፈቅድ ብንኖርም ያን ወይም ይህን እናደርጋለን” ተብሎ የታቀደን ዕቅድ ለመፈጸም በሚደረግ ጥረት ውስጥ የእግዚአብሔርን እገዛ ትልቅ መሣሪያ አድርጎ መጠቀም ግድ ይላል። (ያዕ. ፬፥፲፭)

የንስሓ አባቶችም ይህ አገልግሎት ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጪ የሚፈጸም እንዳይሆን የመምራትና የማስፈጸም ትልቅ ድርሻ አላቸው። ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን ለመቃኘት ያህል፦

. ከመንፈሳዊ ዝለት ማንቃት

የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ከትምህርታቸው ጎን ለጎን በሚኖራቸው ጊዜ በጋራ የሚፈጽሙት አገልግሎት እንደመሆኑ ትዕግሥትን እና ብዙ ጥረትን ይጠይቃል። ነገሮች በተፈለገው ልክ እና ሁኔታ ያለመሄድ ዕድላቸው ሰፊ ከመሆኑ የተነሣ በግለሰቦች ላይ በሚኖር የአገልግሎት ጫና፣ በመርሐ ግብሮች አለመሳካት፣ በቦታ፣ በጊዜ እና በመሳሰሉ ሁኔታዎች አለመመቻቸት ምክንያት በግቢ ጉባኤ አገልግሎት ተሳታፊ በሆኑ ተማሪዎች ዘንድ መባከንን ልናስተውል እንችላለን፡፡ ይህም እንደ አልዓዛር እኅት ማርታ ከአገልግሎት መብዛት የተነሣ መባከን (ሉቃ.፲፥፵) እና ከቃለ እግዚአብሔር እንዲሁም ምሥጢራትን ከመካፈል መራቅ ሊያጋጥሙ የሚችሉ ችግሮች ናቸው።

እነዚህን ችግሮች በመፍታት በኩል ከንስሓ አባት የተሻለ አቅም ያለው አካል ማግኘት አይቻልም። በግቢ ጉባኤው ውስጥ አገልግሎት በመስጠት ላይ ያሉ አባቶች የንስሓ ልጆቻቸው ያሉባቸውን ፈተናዎች ከማንም በተሻለ ያውቃሉና ችግሮቹ ላይ ያተኮሩ የመፍትሔ ሥራዎችን ለመሥራት ትልቁን ድርሻ የመወጣት አቅም አላቸው። በአገልግሎት ላይ ያሉ ተማሪዎች ተስፋ እንዳይቆርጡ በማጽናት፣ በአገልግሎት በመባከን ከሚመጣ መንፈሳዊ ዝለት ከምሥጢራት ሲርቁ እግዚአብሔርን አብነት አድርገው ‘ወዴት አለህ’ (ዘፍ. ፫፥፱) ብሎ መጥራት፣ መፈለግና ማጽናት ይጠበቅባቸዋል፡፡

. እግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ያለው አገልግሎት እንዲፈጽሙ ማስቻል

ቃየን ወንድሙን በመግደል በደል በፈጸመ ጊዜ ፈታሔ በጽድቅ ከሆነ እግዚአብሔር የተፈረደበት ፍርድ ተቅበዝባዥ መሆን ነው። (ዘፍ. ፬፥፲፪) ሊቃውንት አባቶቻችን “ምድርንም ባረስክ ጊዜ እንግዲህ ኃይሏን አትሰጥህም” የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ አድርገው   ተቅበዝባዥነትን በከንቱ መድከም፣ ጀምሮ አለመፈጸም፣ ዘርቶ ፍሬ ማጣት መሆኑን በትርጓሜአቸው አስረድተውናል። የግቢ ጉባኤ አገልጋዮች ድካማቸው ከንቱ አገልግሎታቸውም ፍሬ አልባ እንዳይሆን ዘወትር ራሳቸውን በጸሎት በማነጽ፣ በንስሓ ማንጻት እና ማዘጋጀት ግድ ይላቸዋል።

የንስሓ አባቶች ንስሓን የመቀበል እና የመናዘዝ አገልግሎት ደግሞ በሌላ በማንም ሊተካ የማይችል ነው። በመሆኑም በግቢ ጉባኤ አገልግሎት ተሳታፊ የሆኑ ተማሪዎችን በመናዘዝ እና ከኃጢአት እንዲነጹ በማድረግ ለአገልግሎቱ መሳካት የበኩላቸውን አባታዊ ኃላፊነት ሊወጡ  ይገባቸዋል።

. የአገልግሎቱን ቀጣይነት ማረጋገጥ

የግቢ ጉባኤ አገልጋዮች በእያንዳንዱ የአገልግሎት እርምጃቸው የንስሓ አባቶቻቸውን ተሳታፊዎች ቢያደረጓቸው ከአገልግሎታቸው መሳካት ባለፈ ከእነርሱ በተጨማሪ ሌሎች አገልጋዮች በሚመጡበት ጊዜ የግቢ ጉባኤን አገልግሎት የተረዱ እና አዲሶቹን አገልጋዮች በተሻለ ጎዳና መምራት የሚችሉ አባቶችን ማፍራት ይቻላል። ይህም የማእከላትን ጫና ከመቀነስ ባሻገር አዳዲስ አገልጋዮች አገልግሎቱን ከታች ከመጀመር ይልቅ በየአጥቢያቸው ያሉ የንስሓ አባቶቻቸውን በማማከር ከነበረበት የማስቀጠል እና የማሳደግ ዕድል እንዲያገኙ ያደርጋል።

ተግዳሮቶች

የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎት መረዳት የሚችሉ እና ወርደው ከተማሪዎች ጋር ለመሥራት የመንፈስ ዝግጁነት ያላቸው የንስሓ አባቶች ያስፈልጉናል። የንስሓ አባቶች እና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ቁጥር አለመመጣጠን፣ እስከ አለመግባባት የሚያደርስ ሰፊ የዕድሜ ልዩነት መኖር፣ ለረጅም ጊዜ በገዳማዊ ሕይወት ያለፉ መነኮሳት ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች አባት ሆነው መመደባቸው፣ የቋንቋ ክፍተት መኖሩ፣ ዘመኑን ዋጅቶ በሚገባው ልክ ወጣቱን ለማስተማር እና ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማቅረብ የሚያስችል የትምህርት ዝግጅት የሌላቸው አባቶች በንስሓ አባትነት መመደባቸው እና የመሳሰሉት ምክንያቶች የንስሓ አባቶች በሚፈለገው መጠን በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ውስጥ የሚጠበቅባቸውን በጎ አስተዋጽኦ እንዳያበረክቱ እንቅፋት ሆነዋል።

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የእረኝነት ሥራን የሚሠሩ እነዚህ ካህናት ትሩፋትን እና ትጋትን ገንዘብ ያደረጉ፣ በመንፈስ ብርታት፣ በትምህርተ ሃይማኖት ብስለት እና በተቀደሰ ሕይወት ይጠብቋቸው ዘንድ ከተሾሙላቸው ሰዎች እጅግ ተሽለው መገኘት እንዳለባቸው ሲያስረዳ “በካህኑና በምእመናኑ መካከል ሊኖር የሚገባው ልዩነት አእምሮ ባለው ሰው እና ደመ ነፍሳዊ በኾኑ እንስሳት መካከል ያለውን ያህል የሰፋ ሊሆን ይገባል። የጉዳዩ ክብደት እና አሳሳቢነት እጅግ ታላቅ ነውና” ይላል። የዚህ ዓይነት ጥንቃቄ በተለይ ዘመን በወለዳቸው አምላክ የለሽ እሳቤዎች እና ፍልስፍናዎች፣ በምንፍቅና ትምህርቶች፣ በሰፋፊ የኃጢአት ልምምዶች እና በመሳሰሉት ለመነጠቅ የሰፋ ዕድል ላላቸው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች አባት ሆነው የሚሾሙ ካህናትን በተመለከተ ሲሆን ይበልጥ ምክንያታዊ ይሆናል።

የመፍትሔ ሐሳቦች

የንስሓ አባቶች ኑዛዜን ተቀብሎ ከኃጢአት እሥራት ከመፍታት ባለፈ በግቢ ጉባኤ አግልግሎት ውስጥ ጠለቅ ያለ ተሳትፎ እና የእረኝነት ድርሻ እንዳላቸው መረዳት ይገባቸዋል፡፡ በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ላይ ያሉ ወጣቶችም ዝግጅት ያላቸውን የንስሓ አባቶች የመንፈስ ልጆቻቸውን በተመለከተ በሚወሰኑ ውሳኔዎች እና በሚሠሩ ሥራዎች ላይ ንቁ ተሳታፊዎች እንዲሆኑ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ያስፈልጋል። በመሆኑም በንስሓ አባቶችና በልጆቻቸው መካከል ያለውን ግንኙነት የተከሳሽ እና የዳኛ አስመስሎ የሚያሳየውን ምዕራባዊ ነጽሮት በማራቅ ኦርቶዶክሳዊ በሆነው የሐኪም እና ታካሚ ዓይነት ግንኙነት እሳቤ መነሻነት ጥብቅ የሆነ መረዳዳት እና መግባባት ላይ የተመሠረተ ግንኙነት መፍጠር መቻል ያስፈልጋል፡

ማእከላት እና የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላትም ግቢ ጉባኤያቱ በያሉባቸው አካባቢዎች የሚነገሩ ቋንቋዎችን እና የአካባቢውን ባህል የተረዱ ካህናትን ከዚያው አካባቢ እንዲገኙ በማድረግ በየደረጃው ያሉ መሠረታዊ ችግሮችን ለመቅረፍ ሊሠሩ ይገባል። በተጨማሪም አገልግሎታቸው ንስሓን ከመቀበል ያለፈ እና ሁለንተናዊ የመንፈሳዊ አባትነት አገልግሎት መሆኑን ተረድተው በግቢ ጉባኤያት አገልግሎቶች ውስጥ የበኩላቸውን እንዲወጡ ማንቃትና ይህንን ማድረግ እንዲችሉ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡

ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት

ዓለማየሁ ገብሩ

ትውፊት ማለት አወፈየ ከሚለው የግእዝ ግሥ የመጣ ሲሆን ውርስ፣ ቅብብል ተብሎ ይተረጎማል፡፡ ትውፊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ትምህርቶቿን ጠንቅቃ ከያዘችበት እና ልጆቿንም ከምትመራባቸው ሦስቱ የመሠረተ እምነት ምንጮች ውስጥ አንደኛው ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት ተብለው የሚጠቀሱት፡- ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊት ሲሆኑ እነዚህ መሠረቶች ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሳትለወጥና ሳትበረዝ እንደ ደመቀች ከትውልድ ወደ ትውልድ እንድትተላለፍ አድርገዋታል፡፡

ለቤት መቆም ብቻ ሳይሆን ቤቱ ዕድሜ እንዲኖረውም የሚያደርገው የመሠረቱ ጥንካሬ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ትውፊት አንድ ሰው ከእርሱ በፊት ከነበረው ማኅበረሰብ የሚቀበለውና የሚወርሰው እምነት፣ ባህል፣ የአኗኗር ዘይቤ፣ …ወዘተ ሲሆን ሒደቱም በዚህ ሳያበቃ እርሱም በተራው ለተተኪው የሚያስተላልፈው ነው፡፡

ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ስለ ትውፊት እንዲህ በማለት ማብራሪያ ይሰጣሉ፡-“ትውፊት በቃል ወይም በጽሑፍ ወይም በተግባር እንቅስቃሴ ከአንዱ ወደ ሌላው የሚተላለፍ ታሪክ፣ ትምህርት፣ ባህል፣ ወግና ሥርዓት ነው፡፡ ትውፊት በተጨባጭ በትክክል የተፈጸመ እንጂ ተረት አይደለም፡፡ ከሕገ ልቡና ወደ ሕገ ኦሪት፣ ከሕገ ኦሪት ወደ ሕገ ወንጌል፣ በቅብብሎሽ የመጣ የተወረሰና ለተከታዩ ትውልድ የተላለፈ ነው፡፡ ትውፊት ልማደ ሀገርን ሕገ እግዚአብሔርን ባህለ ሃይማኖትን ሁሉ የሚያጠቃልልና እንደ መንፈሳዊ ሕግ ሆኖ ሊያዝ የሚችል ነው፡፡” ይላሉ (ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ፤ ፈለገ ጥበብ መጽሔት ፪ኛ ዓመት ቁጥር ፲፭/፲፱፻፺፪ ዓ.ም. ገጽ ፲፭)

ትውፊት ከትውልድ ወደ ትውልድ በሦስት መንገዶች የሚተላለፍ ሲሆን፤ እነርሱም፡- የሚዳሰስ፣ የማይዳሰስ እና በቃል ይተላለፋሉ፡፡

ሀ. በሚዳሰስ መንገድ የሚተላለፍ ትውፊት፡-

በሚዳሰስ መንገድ የሚተላለፍ ትውፊት በሆነ ዘመን ተሠርተው አገልግሎት የሚሰጡ አብያተ ክርስቲያናት፣ ንዋየተ ቅድሳት እና ቅዱሳት መጻሕፍትን የመሳሰሉት ቅርጻቸውንና ይዘታቸውን ሳይለውጡ ከትውልድ ወደ ትውልድ ተጠብቀው የሚተላለፉበት የትውፊት መተላለፊያ መንገድ ነው፡፡ እነዚህ ንዋያተ ቅዱሳት በክብር እየተጠበቁ ወደ ቀጣይ ትውልድ ይሸጋገራሉ፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን በትውፊት ምክንያት የሚነቅፉና ትውፊት አያስፈልግም መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ የሚሉ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ በትውፊት ያለንበት ዘመን መድረሱን ይዘነጋሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ መቼ መዘጋጀት ጀመረ? ከሚለው አንስቶ መቼ አሁን ያለበትን ቅርጽ ያዘ እስከሚለው ድረስ ያለውን ብንመረምር ከአንዱ ወደ አንዱ እየተላለፈ በትውፊታዊ መንገድ ቀድሞ የተጻፉትን በመቀበል በየዘመናቱ የሚጻፉትንም ደግሞ በማካተት አሁን ያለበትን መልክ ይዞ እኛ ጋር እንደደረሰ መዘንጋት የለብንም፡፡

ለ. በማይዳሰስ መንገድ የሚተላለፍ ትውፊት፡-

ርእያዊ ትውፊት ሲባል የተለያዩ ባህሎች አከባበር፣ የተለያዩ መንፈሳዊ መዝሙራት ወይም ወረብ አቀራረብ እንዲሁም መንፈሳዊ አለባበስና አመጋገብ የመሳሰሉ በማየት የምንወርሳቸው ወይም የምንቀበላቸው የትውፊት ዓይነቶች ናቸው፡፡ ለዚህ ጥሩ ማሳያ የሚሆነው በሕገ ልቡና ዘመን የአሥራት በኲራት አቀራረብ ሕግ ሆኖ ለሙሴ ከመነገሩ በፊት አበ ብዙኃን አብርሃም፣ ልጁ ይስሐቅና ያዕቆብ ያቀርቡ ነበር፡፡ የመሥዋዕትንም አቀራረብ በማየትና በመስማት ከልጅ ልጅ እየተቀባበሉ ሲገለገሉበት ነበር፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ አሥርቱን ትእዛዛት ከመቀበሉ በፊት ቅዱስ ዮሴፍ ዝሙት ኃጢአት እንደሆነና ከዚያም ሲሸሽ የዝሙት ኃጢአት እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ኃጢአት መሆኑን ዐውቆ ራሱን ሲጠብቅ እናየዋለን (ዘፍ.፴፱፤፱)፡፡ ሕግ ሳይሰጥ ከየት ዐወቀው ከተባለ ከአባቶቹ በማየትና በመስማት የተማራቸው ነገር ስላለ ነው፡፡  እስራኤላውያን የፋሲካል በዓል አከባበር አሁን ድረስ ጥንታዊ ባህሉን ጠብቀው ያከብራሉ፡፡ በዓል አከባበሩ ተጽፎላቸው ሳይሆን በማየት ብቻ ከአንዱ ትውልድ ወደ አንዱ ትውልድ እየተላለፈ የመጣ ስለሆነ ነው፡፡

በአጠቃላይ ትውፊት የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ወጥ ሥርዓት እንዲኖራት የሚረዳ ሲሆን ከዚህ ትውፊታዊ ሥርዓት የሚወጡትን ደግሞ ለይተን እንድናውቅበት ይረዳናል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለን “ዳሩ ግን ማንም ሊከራከር ቢፈቅድ እኛ ወይም የእግዚአብሔር አብያተ ክርስቲያናት እንዲህ ያለ ልማድ የለንም ” (፩ቆሮ.፲፩፤፲፮) በማለት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ውጪ ካሉ ተቋማት እንድንጠበቅ እንዲሁም ሥርዓት፣ ወግ፣ ባህል ከሌላቸው አካላት ጋር መለየታችንን በጉልህ የሚያሳየን መሠረተ እምነት ነው ትውፊት፡፡

ሐ. ቃላዊ ትውፊት፡-

ቅዱስ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ሰዎች ሲያስተምር “አሁንም ወንድሞቻችን ሆይ ጸንታችሁ ቁሙ፤ በቃላችንም ቢሆን ወይም በመልእክታችን ያስተማርናችሁንና የሠራንላችሁን ሥርዓት ያዙ፡፡” (፪ተሰ.፪፥፲፭) ይላል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ከጻፈልን ፲፬ቱ መልእክት በተጨማሪ በቃል የሰበከውንም እንድንይዝ ይመክረናል፡፡ እንደሚታወቀው የክርስቶስ ቤተሰብ የተባሉት ከዋለበት ውለው፣ ካደረበትም አድረው ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብለው ከተማሩት ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ሁለቱ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ዮሐንስ እንዲሁም ከሰባ ሁለቱ አርድእት ደግሞ ቅዱስ ማርቆስና ቅዱስ ሉቃስ ብቻ ናቸው ወንጌልን የጻፉልን፡፡

የተቀሩት ሐዋርያትና አርድዕት የእግዚአብሔርን ቃል አላስተማሩም? አልሰበኩም? አልጻፉም ማለት ነው? አይደለም፡፡ ይህ የሚያሳየው ከላይ ባነሣነው የቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት መሠረት ባይጽፉም ወንጌል መስበካቸውን አንጠራጠርምና በቃል የሰበኩትንም እንድንይዝ ተነግሮናል፡፡ ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ቅዱሳን ሐዋርያት በቃል የሰበኩትን የእነሱ ተከታይ የሆኑና ደቀ መዛሙርቶቻቸው ጽፈው ያስተላለፉትን የምትቀበለው፡፡

ኦርቶዶክሳዊ ቃላዊ ትውፊት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ያስተማራቸውን፣ ሐዋርያትም ለተከታዮቻቸው ያስተላለፉትን እየተቀባበሉ እዚህ እኛ ዘመን ላይ ደርሷል፡፡ “ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና” (፩ቆሮ.፲፩፥፳፫) እንዲል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡፡

ቃላዊ ትውፊት ከጥንት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን በኩል ቃል በቃል ሲነገር የመጣ በቃልም በጽሑፍም ከአበው ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የኖረና የሚኖር ነው፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት ያልተጻፉትን ከአበው ቃል በቃል የተላለፉትን የእምነት፣ የሥርዓት፣ የትምህርትና የታሪክ ውርሶች የሚቀርብበት ነው፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት በቃላዊ ትውፊት አማካይነት በወንጌል ያልተጻፈውን የጌታችን ትምህርት ጌታችን የተናገረው ብለው መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሲጽፉ እናያለን፡፡ ለምሳሌ “ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፀዕ ነው፤ ያለውንም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቃል ዐስቡ፡፡” (ሐዋ.፳፥፴፭) ይላል፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አለ ያለውን ቃል በአራቱም ወንጌል ውስጥ ተጽፎ አናገኘውም፡፡ ከየት አመጣው ብንል ጌታችን ሲያስተምር የሰማውን እንደጻፈ መረዳት ቀላል ነው፡፡

ጌታችንስ በወንጌል ከተጻፉት ውጪ ሌላ ቃል አላስተማረም ብሎ ማሰብ ሞኝነት አይደለምን? ወንጌላውያኑስ ጌታ የተናገረው ሁሉን ጽፈዋል ብሎ ማመኑ አይከብድምን? ስለዚህ አራቱ ወንጌላውያን ያልጻፉት ወይም ያልመዘገቡት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርቶች መኖራቸውን መገንዘብ ይገባል፡፡ ለምሳሌ፡- ተረፈ ወንጌል የሚባሉት እንደ ተአምረ ኢየሱስ፣ ድርሳነ ማኅጠዊ ባሉት ተጽፏ፡፡ ለዚህም ነው ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ “ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ” (ዮሐ.፳፥፴) ያለው፡፡

በተጨማሪም ቅዱስ ጳውሎስ “የታያቸውም እንዲህ ግሩም ነበር፤ ሙሴም እንኳን እኔ ፈርቻለሁ ደንግጫለሁም” ብሎ ጽፎልን እናገኛለን (ዕብ.፲፪፥፳፩)፡፡ ነገር ግን ሊቀ ነቢያት ሙሴ አለ ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ የጻፈልንን ቃል ሙሴ በየትኛውም መጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ ጽፎት አናገኝም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ከየት አመጣው? ካልን በቃል በተላለፈ ትምህርት አግኝቶት ነው፡፡

በተመሳሳይ ቅዱስ ጳውሎስ ሙሴን ስለተቃወሙትና ስለተከራከሩት ሁለቱ ጠንቋዮች ሲናገር የጠንቋዮቹን መጠሪያ ስም “ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደተቃወሙት” በማለት ይጠቅሳል፡፡ (፪ጢሞ.፫፥፰)፡፡ ይህ ታሪክ በተመዘገበበት በኦሪት ዘጸ. ፯፥፲፩ ላይም ሆነ በሌላ የኦሪት መጽሐፍት ላይ የእነዚህ ሁለት ጠንቋዮች ስም የተገለጸበት ቦታ የለም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ግን ከነስማቸውን ጠቅሶ ይነግረናል፡፡ ከየት አምጥቶት ስማቸውን ጻፈ ብንል በቃላዊ ትውፊት በተላለፈ ትምህርት መሆኑን እንረዳለን፡፡

የሐዋርያትን የቃል ስብከት በተመለከተ የሚናገሩት ቃል የእግዚአብሔርን ቃል እንጂ ከራሳቸው አመንጭተው እንዳልሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲነግረን እንዲህ ይላል፡፡ “ስለዚህም የመልእክትን ቃል እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ከእኛ በተቀበላችሁት ጊዜ በእውነት እንዳለ በእናንተ በምታምኑ ደግሞ እንደሚሠራ እንደ እግዚአብሔር ቃል እንጂ እንደ ሰው ቃል አድርጋችሁ ስላልተቀበላችሁት እኛ ደግሞ እግዚአብሔርን ሳናቋርጥ እናመሰግናለን” (፩ተሰ. ፪፤፲፫)፡፡

“ጐልማሶች ሆይ፥ ክፉውን ድል ነሥታችሁታልና እጽፍላችኋለሁ” /፩ኛ ዮሐ. ፪፥. ፲፫/፡፡

በጥበበ ሲሎንዲስ

ቅዱስ ዮሐንስ “ጐልማሶች ሆይ፥ ክፉውን ድል ነሥታችሁታልና እጽፍላችኋለሁ” በማለት ክፉውን ዓለም ድል የነሡትን ጐልማሶች ያሞግሳቸዋል፡፡ ይህም በክፉ ዓለም እየኖሩ ክፉውን ማሸነፍ መንፈሳዊ ጥንካሬንና ድል መንሣትን ያመለክታል፡፡ አንዳንድ ወጣቶች ‘በወጣትነት ዘመን ላይ እየኖሩ ቅዱስ መሆን እንዴት ይታሰባል? በዓለም እየኖሩ ጻድቅ መሆን እንዴት ይሞከራል?’ ይላሉ፡፡ ነገር ግን በክፉው ዓለም ኖረው ዓለምን ድል መንሣት እንደሚቻል ከጐልማሳው (ወጣቱ) ዮሴፍ ታሪክ እንማራለን፡፡

ዮሴፍ በገዛ ወንድሞቹ ተሸጦ፣ ከሀገሩ ከነዓን ርቆ በግብፅ ባርነት ሲኖር የመጣበትን ፈተና በመቋቋም ክፉን ድል ነሥቷል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “የጌታው ሚስት ዐይኗን ጣለችበት፤ አፍ አውጥታም፣ ‘አብረኸኝ ተኛ’ አለችው”(ዘፍ. ፴፱፥፯)፡፡  ልትይዘውም በሞከረች ጊዜ ዮሴፍ  “እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? በእግዚአብሔር ፊት እንዴት ኃጢአትን እሠራለሁ?” በማለት ልብሱን ጥሎላት እንደሸሸ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ /ዘፍ. ፴፱፥፰-፱/፡፡

ዮሴፍ እንዲህ ዓይነት እርምጃ መውሰዱ ከፍተኛ ዋጋ አስከፍሎታል። የጲጥፋራ ሚስት ልትበቀለው ፈለገች። በመሆኑም ወዲያውኑ እየጮኸች አገልጋዮቹን መጣራት ጀመረች። ዮሴፍ ሊደፍራት እንደሞከረና እርሷ ስትጮኽ ሸሽቶ እንዳመለጠ ነገረቻቸው። ዮሴፍን ለመወንጀል ባሏ እስኪመለስ ድረስ ልብሱን ይዛ ቆየች። ጲጥፋራ ወደ ቤት ተመልሶ ሲመጣ ያንኑ ውሸት ደግማ ተናገረች፤ ጲጥፋራ ይህን ባዕድ ሰው ወደ ቤት በማምጣቱ ለደረሰባት ነገር ተጠያቂው እርሱ እንደሆነ በተዘዋዋሪ ገለጸች። ጲጥፋራም ተቆጣ፡፡ ዮሴፍም ወደ ወኅኒ ተጣለ፡፡ የጲጥፋራ ሚስት አሳዛኝ ታሪክ እንዲህ ያለውን ክፋት አስከትሎአል፡፡

ዮሴፍ ግን ለራሱም፣ ለአለቃውም፣ ለፈጣሪውም የታመነ መሆኑን በተግባር አስመሠከረ፡፡ የዛሬ ወጣቶች ለምንሠራበት ተቋም፣ ለአለቃችን፣ ለጓደኛችን ታማኞች ነን? የአደራ ጥብቅነት ከሰማይ ርቀት ጋር ተነጻጽሮ በሚነገርበት ማኅበረሰብ መካከል አድገን ታማኞች መሆን አለመቻላችን ምክንያቱ ምን ይሆን? ዮሴፍ ዓለም በኃጢአት ስትፈትነው በወጥመዷ ላለመያዝ እግዚአብሔርን አስቧልና በሐሰት ወንጅለውና ወደ ወህኒ እንዲጣል አድርገው ለመከራ በዳረጉት ጊዜ እግዚአብሔር እርሱን አሰበው፡፡ ስደተኛው ዮሴፍ የግብፅ ሹመኛ ሆነ፡፡ እኛም “መንገዴንና አካሄዴን እንደ ቃልህ አቅና፤ ኀጢአትም ሁሉ ድል አይንሳኝ፡፡” ብለን እንጸልይ /መዝ.፻፲፰፥፻፴፫/፡፡

የወጣትነት ዘመን የብርታት ዘመን ነው፡፡ አባቶቻችን ‘በወጣትነት የለቀሙትን እንጨት በስተርጅና ይሞቁታል’ ይላሉ፡፡ የወጣትነት ዕድሜ ሰው ሠርቶ ማግኘት፣ ወድቆ መነሣት የሚችልበት ወቅት ነው፡፡ “አንተ ጐበዝ፥ በጒብዝናህ ደስ ይበልህ፥ በጒብዝናህም ወራት ልብህን ደስ ይበለው፥ በልብህም መንገድ፥ ዐይኖችህም በሚያዩት ሂድ፤ ዳሩ ግን ስለዚህ ነገር ሁሉ እግዚአብሔር ወደ ፍርድ እንዲያመጣህ ዕወቅ፡፡ ሕፃንነትና ጒብዝና፥ አለማወቅም ከንቱ ናቸውና ከልብህ ቊጣን አርቅ፥ ከሰውነትህም ክፉ ነገርን አስወግድ፡፡” እንዲል (መክ. ፲፩፥፱-፲)፡፡

ወጣትነት ብዙ ተስፋ ያለው የሕይወት ክፍል ነው፡፡ በአንድ ዕድል አለመሳካት እንደገና ከመሞከር አይቆጠብም፡፡ ወጣትነት ደስ ይላል፤ ሲያዩት ያምራል፡፡ ምንም ዓይነት ሰው ሠራሽ መዋቢያዎችን ባይጠቀሙም ወጣትነት ውበት ነው፡፡ ደግነትና ክፋት ግን ምርጫ ነው፡፡ ኃጢአትን የሚያስጥለን ዕድሜ ሳይሆን የእግዚአብሔር ፍቅር ነው፡፡ ራስን፣ ታሪክን፣ ሀገርን፣ ሕዝብን ለመለወጥ የሚያስፈልገው ትልቅ ዕድሜ ሳይሆን ትልቅ ልብ ነው፡፡ ዋናው ብዙ ዘመን መቆየታችን ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ መኖራችን ነው፡፡ ባለን ጥቂት ዘመን ለዘመን የሚተርፍ፣ ለትውልድ የሚነገር ነገር መሥራት ይቻላል፡፡

ወጣትነት እንደ እሳት ብርቱ ነው፡፡ ይህ እሳት በአዎንታዊ መንገድ ሲገለጥ ተነሣሽነትን፣ ትኩስነትን፣ ባለ ራእይነትን ያመለክታል፡፡ ይህ እሳት በአሉታዊ መንገድ ሲገለጥ ደግሞ ቍጣን፣ ችኩልነትን፣ አለመታገሥን፣ ስሜታዊነትን፣ ንዴትን ማለትን ያመለክታል፡፡

እሳት በረከት እንደሆነ ጥፋትም ሊሆን ይችላል፡፡ የሚጠቅሙ ነገሮች በአግባቡ ካልተያዙ የሚያጠፉት የጥቅማቸውን ያህል ነው፡፡ እሳት ሆነው ለመጡብን ውኃ ሆነን ማብረድ ይገባል፡፡ በሥጋ መሻት፣ በፍትወት ልብ ሲመጡብን በቅድስና፣ በፈሪሃ እግዚአብሔር ማብረድና ወደ ንስሓ መጋበዝ ይገባናል፡፡ እሳትነታችን የሚያበስል እንጂ የሚያሳርር እንዳይሆን ውኃነታችንም የሚያመጣጥን እንጂ የሚያጠፋ እንዳይሆን መገምገም አለብን፡፡ “እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ ትጸልዩም ዘንድ በመጠን ኑሩ” እንዲል (፩ኛ ጴጥ. ፬፥፯)፡፡

በመጠን መኖር የኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ጠባይ ነው፡፡ ይኸውም “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣህን ዐስብ” የሚለውን መመሪያ ለመጠበቅ ይጠቅማል (መክ.፲፪፥፩)፡፡ ፈጣሪው እግዚአብሔርን የሚያስብ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት ሰው የሚከፋበትን አይናገርም፣ በሰዎች መካከል መለያየትን አይፈጥርም፣ ወላጆቹን አያሳዝንም፣ ጎረቤቶቹን አያውክም፣ ምስኪኖችን አያሳቅቅም፣ የሰዎችንም ክብር አይነካም፡፡

ልበ አምላክ ዳዊት “ጐልማሳ መንገዱን በምን ያቀናል? ቃልህን በመጠበቅ ነው፡፡” በማለት እንደተናገረ (መዝ. ፻፲፰፥፱) ጐልማሶችን በቃለ እግዚአብሔር እንዲበረቱ ማስተማርና መንገድ መምራት ያስፈልጋል፡፡ ወጣቶች ንግግር ስለተማሩ፣ ገንዘብ አያያዝ ስላወቁ፣ የምስክር ወረቀት ስለያዙ ብቻ የሕይወት ብስለት አላቸው ማለት አይደለም፡፡ በታላላቅ ተቋማት ስለሠሩም ታላቅ ሆኑ ማለት አይደለም፡፡ ስለዚህ ታዋቂዎች ብቻ እንዲሆኑ ጥረት ከማድረግ ይልቅ አዋቂዎች እንዲሆኑ ማገዝ ይገባል፡፡ ለዚህም ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ “የእግዚአብሔር ቃልም በእናንተ ዘንድ ጸንቶ ይኖራልና” በማለት እንደተናገረው ከሥጋዊ አስተሳሰብና ድርጊት ርቀው የእግዚአብሔርን ቃል የሕይወት መመሪያቸው አድርገው እንዲጓዙ መርዳት ያስፈልጋል፡፡

በልጅነታችን ጭቃ አቡክተን እንጫወት ነበር፡፡ በዚያም ደስ ይለን ነበር፡፡ ካደግን በኋላ ግን ጭቃን እንኳን በእጃችን ልንነካው በእግራችን ልንረግጠው እንጸየፈዋለን፡፡ ምክንያቱም ማደግ ያስገኘልን ዕውቀት ከጭቃ ከመቆሸሽ በቀር ምንም አይገኝም የሚል ነው፡፡ እንዲሁም በአእምሮ ሕፃን በነበርንበት ዘመን በኃጢአት ለመደሰት ሞክረናል፡፡ ተደልለንም አልፈናል፡፡ ለመንፈሳዊ አካለ መጠን ስንደርስ ግን ከኃጢአት ከመርከስ በቀር ምንም እንደማይገኝ ይገባናል፡፡ ደግሞም ኃጢአትን ልንተው የሚገባን ቅጣቱን ማለትም በሥጋ እስር ቤትን፣ በነፍስ ገሀነመ እሳትን ፈርተን ብቻ ሳይሆን የንጹሐ ባሕርይ እግዚአብሔር ክቡር ፍጥረት ነኝ፣ የክርስቶስ ተከታይ ክርስቲያን ነኝ፣ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ቤተ መቅደስ ነኝ ብለን መሆን አለበት፡፡

በተረፈ ወጣቶች ሆይ! እናንተ ያወቃችሁት በዓለም ላይ ያለው ብቸኛ ዕውቀት አይደለምና፣ ደግሞም ዕውቀት በየዘመኑ ያድጋልና ሌሎችን ለመስማት ፈቃደኛ ሁኑ፡፡ እስከ ዘለዓለም የምንማር ነንና በሃያና በሠላሳ ዓመት ዕውቀትን ጠነቀቅናት ብላችሁ አታስቡ፡፡ በኃይል ሁሉን እቀይራለሁ ከሚል አስተሳሰብ ውጡ፡፡ ይህች ዓለም የወጣቶች ብቻ ሳትሆን የሕፃናትም፣ የጎልማሶችም፣ የአረጋውያንም ዓለም ናትና ለሌላው ዕድል ስጡ፡፡ ሕይወት ረጅም መንገድ እንጂ በአንድ ትንፋሽ የምትጠናቀቅ አይደለችምና በእርጋታና በማስተዋል መጓዝን አትርሱ፡፡ ያን ጊዜ “ጐልማሶች ሆይ፥ ክፉውን ድል ነሥታችሁታልና እጽፍላችኋለሁ” የሚለው መልእክተ ጽድቅ ይደርሳችኋል፤ የድል አክሊል ይዘጋጅላችኋል፤ የመንግሥተ ሰማያት በር ክፍት ይሆንላችኋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የደረጃ ሦስት መምህራን ሥልጠና ለመጀመሪያ ጊዜ ተሠጠ

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የአቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል የደረጃ ሦስት የግቢ ጉባኤያት መምህራን ሥልጠና ለመጀመሪያ ጊዜ ከጥቅምት ፱ እስከ ፲፮ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም መስጠቱን አስታወቀ፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን አዳራሽ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ባፈራቻቸው መምህራን ለአንድ ሳምንት ሲሰጥ በቆየው ሥልጠምና ዐርባ የግቢ ጉባኤያት መምህራን የተሳተፉ ሲሆን፤  ነገረ ሃይማኖት፣ ነገረ ድኅነት፣ አንፃራዊ ትምህርተ ሃይማኖት፣ የመጻሕፍት ትርጓሜያት አጠናን ስልት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ትምህርት አበው በሃይማኖተ አበው እና አርአያነት ያለው የመምህራን ሕይወት በሚሉ ርእሶች ላይ በማተኮር ተሰጥቷቸዋል፡፡

ይህ የደረጃ ሦስት መምህራን ሥልጠና ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰጠ እንደመሆኑ መጠን የቡድን ውይይት፣ የእርስ በእርስ የልምድ ልውውጥም አድርገዋል፡፡ በተጨማሪም አገልግሎት ላይ ተሰማርተው እያገለገሉ እንደመገኘታቸው ሳምንቱን ሙሉ ምሽቱን በአገልግሎት ላይ ሰፊ ልምድ ያላቸው መምህራን እየተገኙ ልምዳቸውን አካፍለዋል፡፡

ሥልጠናውን በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የአቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል የተዘጋጀ ሲሆን፤ ደረጃ አንድ የመምህራን ሥልጠና በማእከላት፣ ደረጃ ሁለት ደግሞ በማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች አማካይነት ይሰጣሉ፡፡ ፣ ደረጃ ሦስትን ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ በዋናው ማእከል የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ እንዲሰጥ በተወሰነው መሠረት ሥልጠናው ተካሂዷል፡፡

በዚህ ሥልጠናም ሠልጣኞች ሰፋ ያለ ትምህርት እና ልምድ መቅሰማቸውን በመግለጽ በሚሄዱበት ሁሉ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚያገለግሉ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል፡፡

ከፊት ይልቅ ትጉ (፪ኛ.ጴጥ. ፩፥፲)

በመጋቤ ሃይማኖት /  ምትኩ አበራ

ይህንን ኃይለ ቃል የተናገረው ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ነው፡፡ ኃይለ ቃሉን የምናገኘው ደግሞ በ፪ኛ ጴጥ. ፩፥፭-፲፩ ላይ ነው፡፡ ሙሉው ንባብ እንዲህ ይላል፡- “… ስለዚህ ምክንያት ትጋትን ሁሉ እያሳያችሁ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፤ በበጎነትም ዕውቀትን፤ በዕውቀትም ራስን መግዛት፤ ራስንም በመግዛት መጽናትን፤ በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰል፤ እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማችን መዋደድ፤ በወንድማማችም መዋደድ ፍቅርን ጨምሩ፤ እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ሆነው ቢበዙ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ዕውቀት ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንዳትሆኑ ያድርጉአችኋልና፡፡ እነዚህ ነገሮች የሌሉት ዕውር ነውና በቅርብ ያለውን ብቻ ያያል የቀደመውንም ኃጢአቱን መንጻት ረስቷል፡፡ ስለዚህ ወንድሞች ሆይ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ …”

ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በጥሞናና በእርጋታ ካነበብን በኋላ መልእክቱን በጥልቀት መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ርእሱን እናስተውል “ከፊት ይልቅ ትጉ” ነው የሚለው፡፡ እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ በዚህ ርእስ ሦስት ነገሮችን ብቻ እናያለን፡፡ እነርሱም፡-

፩. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባሉት እነማን ናቸው?

፪. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባልንባቸው የትጋት አቅጣጫዎች ምንድናቸው?

፫. የተባልነውን በማድረጋችን የምናገኘው ምንድነው? የሚሉት ናቸው፡፡

. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባሉት እነማን ናቸው?

ኃይለ ቃሉን በአስተውሎት ስንመለከተው ትጉ ብቻ ሳይል “ከፊት ይልቅ ትጉ” ነው የሚለው፡፡ ይህ ማለት ከትጋት በአፍአ ሆነው የሚያንቀላፉትንና በስንፍና ሰንሰለት ታስረው በተስፋ መቁረጥ ምንጣፍ የተኙትን አይመለከትም ማለት ነው፡፡ ይህ ማለት በትጋት ውስጥ ሆነው የአቅማቸውን እያከናወኑ ላሉት ትጉኀን ክርስቲያኖች የተነገረ ነው ማለት ነው፡፡ ሐዋርያው ትጋታቸውን ተቀብሎና አክብሮ ነው የሚጽፍላቸው ትጋታችሁ ጥሩ ነው፣ ግን ብቻውን በቂ አይደለም ይላቸዋል፡፡ አሁን በትጋታቸው ላይ ትጋትን እንዲጨምሩ ቀድሞ ከነበራቸው ትጋት በተጨማሪ የበለጠ እንዲተጉ ሲመክራቸው “ከፊት ይልቅ ትጉ” ይላቸዋል፡፡ ይህም ማለት ቀድሞ ይጾሙ፣ ይጸልዩ፣ ያገለግሉ ከነበረበት ትጋታቸው በተጨማሪ የበለጠ እንዲተጉ ይመክራቸዋል ማለት ነው፡፡

የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች እኛስ እንዴት ነን? እየጾምን ነው? በጸሎታችንስ እንዴት ነን? የማያቋርጥ የዕለት ተዕለት ጸሎት ይኖረን ይሆን? እንዲያው ለመሆኑ ከፊት ይልቅ እየተጋን ነው? ወይስ ከነአካቴው በመንፈሳዊ አገልግሎታችን ዝለናል? ምላሹ የራሳችሁ ሆኖ ለራሳችሁ ነው፡፡ ይኼኔ እኮ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከፊት ይልቅ ትጉ እያለ እንኳንስ ከፊት ይልቅ ልንተጋ መደበኛውንና የሚጠበቅብንን ክርስቲናዊ ግዴታችንን እና የአገልግሎት ድርሻችንን በአግባቡ መወጣት የተሳነን ሞልተናል፡፡ ብቻ ፈጣሪ ለሁላችንም ልቡና ይስጠን፡፡

. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባልንባቸው የትጋት አቅጣጫዎች ምንድናቸው?

እጅግ የተወደዳችሁና የተከበራችሁ አንባብያን እስቲ አንድ ጊዜ ቀና በሉና ወደ መነሻ(መሪ) ምንባባችን ተመለሱ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በቁጥር ፲ ላይ “…መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ተጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ…” ብሎ ከመጀመሩ በፊት ከላይ እንድናነባቸውና እንድንተጋባቸው የሚያስፈልጉ ዋና ዋና ጉዳዮችን በዝርዝር አስቀምጧል፡፡ እነዚህ ጉዳዮች ስምንት ሲሆኑ፤ እነርሱም፡-

፩. እምነት                           ፭. መጽናት

፪.በጎነት                              ፮. እግዚአብሔርን መምሰል

፫. ዕውቀት                           ፯. የወንድማማች መዋደድ

፬. ራስን መግዛት                 ፰. ፍቅር ናቸው፡፡

እያንዳንዱ ክርስቲያን እነዚህን ሰፍሮና ቆጥሮ ዘወትር በሕይወቱ ውስጥ እየፈለገ ምን አለኝ? ምንስ ይቀረኛል? በማለት በትጋት እያሰላ መኖር ይገባዋል፡፡

በአርባና በሰማኒያ ቀን ከሥላሴ የጸጋ ልጅነትን ገንዘብ ያደረገ አንድ ክርስቲያን በቅድሚያ እምነት ሊኖረው ግድ ነውና ሐዋርያው በእምነት ጀመረ፡፡ እምነት ወይም ሃይማኖት ስንል ልክ እንደ አንድ ሳንቲም ሁለት አስፈላጊ ገጽታዎችን የያዘ መሆኑን ማወቅና መረዳት ያስፈልጋል፡፡ እነሱም ማመንና መታመን ይባላሉ፡፡ አንድ ክርስቲያን ሃይማኖት ወይም እምነት አለኝ ሲል በፈጣሪዬ አምናለሁ እታመንማለሁ ማለቱ ነው፡፡ ማመን ማለት ለዚህች ዓለም ሠራዒ ወመጋቢ አላት ብሎ ማመን ሲሆን መታመን ማለት ደግሞ አለ ብለን ለምናምነው አምላክ መገዛት፣ እሺ በጀ ማለት በሕጉና በትእዛዙ መጓዝ ማለት ነው፡፡ በጥቅሉ ሃማኖትና ሥነ ምግባርን ይዞ መገኘት ማለት ነው፡፡

የአንድ ክርስቲያን እምነቱ በየጊዜው ያድጋል፡፡ ይህ ማለት የማመኑና የመታመኑ ጥበብ እየተረዳው (እየገባው) ሲመጣና ራሱን ለፈጣሪና ለሕጉ ማስገዛት ሲጀምር ማመኑና መታመኑም እየጨመረ ይሄዳል ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “ስለዚህ ምክንያት ትጋትን ሁሉ እያሳያችሁ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፣ …” ብሎ ከእምነት የጀመረው፡፡ ሰው አማኝ ሆኖ የበጎነት ድርቅ ካጠቃው ደግሞ ዋጋ የለውም፡፡ አንዳንድ ሰዎች ለምሳሌ በአጽዋማት ጊዜ ውሎ ቅዳሴ እያስቀደሱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ይህ እኔ የምቆምበት ቦታዬ ነው እያሉ በቦታ የሚጣሉ ከሆነ እምነታቸው በውስጡ በጎነትና ቅንነት ይጎድለዋል ማለት ነው፡፡

አንዳንዱ ደግሞ በጎነት ይኖረውና በጎነቱ ግን ያለ ዕውቀት ሆኖ ይጎዳዋል፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ ሰዎች በበጎነታቸው ገንዘባቸውንና ዕውቀታቸውን የቤተ ክርስቲያንን እምነትና ሥርዓት ለማፍረስ ለቆሙ መናፍቃንና የውስጥ ጠላቶች ሲያውሉ ይታያል፡፡ ባለማወቅ የረዱ እየመሰላቸው ማለት ነው፡፡ በረከታቸው ይድረሰንና በአንድ ወቅት የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ “ሃይማኖት ያለ ዕውቀት ጅልነት ነው፤ ዕውቀት ያለ ሃይማኖት እብደት ነው” ይሉ ነበር፡፡ ስለዚህ ነው ሐዋርያው “በእምነታችሁ ላይ ዕውቀትን ጨምሩበት” ያለው፡፡

በዕውቀት ላይ ደግሞ ራስን መግዛት እንድንጨምር ታዘናል፡፡ ምክንያቱም በራስ መግዛት መሪ ያልተዘወረ ዕውቀት የዲያብሎስ ዕውቀት ነው፤ ያስታብያል፣ ወደ እንጦሮጦስም ያስወርዳል፡፡ በራስ መግዛት ላይ መጽናትን ጨምሩበት ካላ በኋላ እንደገና በመጽናት ላይ እግዚአብሔርን መምሰል ጨምሩበት ይለናል፡፡ አንዳንድ ሰዎች “እኔ እግዚአብሔርን ብሆን ኖሮ እንዲህና እንዲያ አደርግ ነበር” እያሉ ሲዝቱ ይስተዋላል፡፡ እግዚአብሔርን መሆን ለመፍለጥና ለመቁረጥ ወይም ለማጥፋትና ለመቅሰፍ ብቻ የሚመስላቸው ናቸው፡፡ ግን እኮ እግዚአብሔርን መሆን ውስጥ በጥፊ መመታትና መሰቀል መሸከምም አለ፡፡ ኧረ እንደውም “የማያውቁትን ያደርጋሉና ይቅር በላቸው” ማለትም አለበት፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔርን መምሰል ማለት ሆደ ሰፊ፣ ነገር አላፊ፣ ይቅር ባይ፣ ቻይና ታጋሽ መሆን ስለ ሌሎች ራስን አሳልፎ መስጠት ማለት መሆኑን ልብ ልንል ያስፈልጋል፡፡ እስኪ ቆም ብለን ራሳችንን እንመርምር፡፡

ሐዋርያው አላበቃም እግዚአብሔርን በመምሰል ላይ የወንድማማች መዋደድን ጨምሩበት ማለትም የሰፈሬ፣ የመንደሬ፣ የእናትና አባቴ … ከሚለው የወጣ የመጀመሪያውን ሰው አዳምን መሠረት ያደረገ ወንድማማችነትን ገንዘብ አድርጉ ማለቱ ነው፡፡ በዚህ የወንድማማች መዋደድ ላይ ፍቅርን ጨምሩ ይለናል፡፡ ፍቅር ምንድነው? ፍቅር እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔርን ምስክር ያደረገ ከሸፍጥና ከጨለማ ሥራ የጸዳ፣ ፍቅርን ያዙ ሲለን ነው፡፡ አንድም ፍቅር በቅዱስ ጳውሎስ አስተምህሮ (፩ኛቆሮ. ፲፫) የሚታገሰውን፣ የማይቀናውን፣ የማይመካውን፣ የማይታበየውን፣ የማይበሳጨውን፣ ከእውነት ጋር ደስ የሚለውን ቸርነት የሚያደርገውን፣ … ንጹሑን ፍቅር ገንዘብ አድርጉ ይለናል፡፡

የተወደዳችሁ አንባብያን እነዚህን ከላይ የተዘረዘሩትን ስምንቱን ዋና ዋና ቁም ነገሮች ሁል ጊዜ በሕይወታችን ውስጥ እንፈልጋቸው፤ ጨምሩ እየተባልን አንዱን ይዘን ለሌላው እንድንተጋ ታዘናል፡፡ እስኪ ቆም ብለን እናስብ፡፡ በእያንዳንዳችን ሕይወት ከስምንቱ ስንቱ አሉ? ስንቱን ይዘን ስንቱ ይቀረናል? እነዚህ የክርስትናችን ትጋት አቅጣጫዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የመንፈሳዊ አገልግሎታችን ማኅቶታት(መብራቶች) ናቸው፡፡ ስለዚህ ዘወትር በትጋት እንፈልጋቸው፡፡ አንዱን በአንዱ ላይ ለመጨመር እንትጋ ፈጣሪያችን መትጋትን ያድለን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

. የተባልነውን በማደረጋችን የምናገኘው ምንድነው?

የተወደዳችሁና የተከበራችሁ አንባብያን እንግዲህ ከላይ እንዳስቀመጥነው ስምንቱን የትጋት አቅጣጫቻዎቻችንን ተከትለን ባለን የቀድሞ ትጋታችን ላይ እነዚህን ገንዘብ ለማድረግ ዘወትር በትጋት ላይ ትጋት እያሳየን ከቀጠልን ምን እንደምናተርፍ ሐዋርያው በአጭር አገላለጥ አስቀምጦልናል፡፡ እንዲህ ሲል “እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ሆነው ቢበዙ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ዕውቀት ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንዳትሆኑ ያደርጓችኋልና”(ቁ.፰)፡፡

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱትን ስምንቱን ቁም ነገሮች እየጨመርንና እያበዛን ከሄድን ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንደማንሆን በግልጽ ቋንቋ ነግሮናል፡፡ ሥራ ፈትና ፍሬ ቢስ የሚሉት ቃላቶች ሁለት ቢሆኑም ግን አንድ ናቸው፡፡ አንዱ አንዱን ይስበዋል፤ ማለትም ሰው ሥራ ፈት ሲሆን ነው ፍሬ ቢስ የሚሆነው፡፡ ፍሬ ያለ ሥራ እንደማይገኝ ሁሉ ፍሬ ቢስነትም ያለ ሥራ ፈትነት አይኖርም፡፡

ሥራ ፈትነት በሁለቱም ዓለማት ከባድ ቢሆንም በተለይ በመንፈሳዊው ዓለም ትንሽ ለየት ይላል፡፡ “ሥራ የፈታ አእምሮ የሰይጣን ቤተ ሙከራ ይሆናል” የሚል አባባል አለ፡፡ በማቴዎስ ወንጌል ምዕ.፲፪ ላይ እርኩስ መንፈስ ከሰው እንደሚወጣ (ማውጣት እንደሚቻል) ይነግረንና በዚያው ምዕራፍ ላይ “ተመልሶ ይመጣል” ይለናል፡፡ ይህንን የሐዲስ ኪዳን መተርጉማን ሲያብራሩት ከወጣ በኋላ ተመልሶ የማደር ሥልጣን የለውም ዳሩ ግን ማሰቡ አይቀርም፡፡ ሲያስብ ግን ያ ሰው ከጾም ከጸሎት በአፉ ሆኖ ከመንፈሳዊ ሕይወቱ ከመልካም ሥራው ተዘናግቶ(ተታሎ) ቢያገኘው፡- እንዲህ ይለናል፡፡ “…ወደወጣሁበት ቤቴ እመለሳለሁ ይላል ቢመጣም ባዶ ሆኖ ተጠርጎና አጊጦ ያገኘዋል፤ ከዚያ ወዲያ ይሄድና ከእርሱ የክፉትን ሰባት ሌሎችን አጋንንት ከእርሱ ጋር ይወሰዳል፤  ገብተው በዚያ ይኖራሉ፡፡ ለዚያ ሰው ከፊተኛው ይልቅ የኋለኛው ይብስበታል …” (ማቴ.፲፪፥፵፬-፵፭)፡፡

እንግዲህ ልብ አድርጉ የሥራ ፈት አእምሮ ለሰይጣን የተጠረገና ያጌጠ ቤቱ መሆኑን እየነገረን ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሥራ ፈቶች ብዙ ይነግረናል፡፡ ሥራ ፈቶች የራሳቸውን ነፍስ ከማስኮነን አልፈው ለሌሎች ሰዎችም ጭምር አዋኪዎች ናቸው፡፡ አይሁድ እንኳን በአቅማቸው የሚፈልጉትን ተንኮል ከግብ ለማድረስ ሥራ ፈቶችን ይጠቀሙባቸው ነበር፡፡ ለምሳሌ በአንድ ወቅት ሐዋርያው ጳውሎስን በተቃወሙት ጊዜ እነዚህኑ ሥራ ፈቶች እንደተጠቀሙባቸው መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ “… አይሁድ ግን ቀንተው ከሥራ ፈቶች ክፉ ሰዎችን አመጡ፣ ሕዝቡንም ሰብሰው ከተማውን አወኩ” (ግ.ሐዋ.፲፯፥፭)፡፡

በዚህ በሥጋዊው ዓለም እንኳን ክፉ ሰዎች የክፋታቸውን ጥግ ለመግለጥና ለማሳየት በፈለጉ ጊዜ የሚጠቀሙባቸው እነዚህኑ ሥራ ፈቶችን ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓለምም ቢሆን በተቻለን መጠን ሥራ ፈት ላለመሆን መትጋት አለብን፡፡ ሥራ ማለት ከቀጣሪው አካል የምንታደለው ብቻ ግን አይደለም፡፡ ራሳችን ለራሳችን ሥራ ልንሰጠው ይገባል፡፡ ለምሳሌ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማነበብ፣ መጠየቅ፣ ለመረዳት መጣር ገዳማትንና አድባራትን እየሄዱ እጅ መንሳት፣ ማስቀደስ፣ በሰርክና በልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያን ታላላቅ የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብራት ላይ እየተገኙ መማር በሰንበት ት/ቤትና በመንፈሳዊ ማኅበራት ውስጥ ማገልገል … ወዘተ፡፡

የተወደዳችሁ አንባብያን ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ከላይ ያስቀመጣቸውን ስምንት ቁም ነገሮች በመሰብሰብ ከተጠመዳችሁ ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች አትሆኑም ብሎናል፡፡ ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች ካልሆንን ደግሞ የሰይጣን መፈንጫ አንሆንም ማለት ነው፡፡ እንዲህ ከሆንን ደግሞ በመጨረሻ ጊዜ በኃጥአን ሊፈርድባቸው፣ ለጻድቃን ሊፈረድላቸው የሚመጣው አምላካችን “ሑሩ እምኔየ ሳይሁን ንዑ ሀቤየ ቡሩካኑ ለአቡዬ፤ እናንት የአባቴ ቡሩካን ኑ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያዘጋጀሁላችሁን መንግሥተ ሰማያትን ውረሱ” ይለናል፡፡ ይህ እንዲሆን ግን ከፊት ይልቅ እንትጋ፡፡

ትጉኁ አምላካችን ትጋቱን ያድለን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ አሜን፡፡