ዘረኝነት፡ የዘመናችን ወጣቶች ተግዳሮት

በአዱኛ ጌታቸው

ክፍል አንድ

መግቢያ

እንደ ማኅበራዊ ሳይንስ ተመራማሪዎች የወጣትነት ዘመን የሽግግር ዘመን ነው፡፡ ይህ ሽግግር በሁለት ይመደባል፡፡ አንደኛው ከልጅነት ወደ ጎልማሳነት የሚሸገጋሩበት ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ከቤተሰብ ጥገኝነት ራስን ወደ መቻል የሚሸጋገሩበት ዘመን ነው፡፡ ይህ የሽግግር ዘመን ወጣቶች ጊዜያቸውን በማስተዋል ከመሩት ለፍሬ የሚበቁበት በማስተዋል ካልመሩት ደግሞ ለጥፋትና ለውድቀት የሚደራጉበት ጊዜ ነው፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ ስለ ወጣትነት ዘመን ሲናገሩ “በአበባ ውስጥ የፍሬ እንቡጥ ለመያዝ መጀመሪያ የአትክልቱ አያያዝ ደንበኛ ሆኖ ሲገኝ ይጠቅማል፡፡ ወጣትም ከፍሬ ለመድረስ የሚችለው በወጣትነቱ በሠራው ሥነ ምግባር ነው፡፡ ወጣት ሰውነቱን በቆሻሻ ምግባር ያቆራመደው እንደሆነ ተስፋ ይቆርጣል፡፡ ያቀደውም ነገር ከመንገድ ይመለሳል፡፡ መንፈሳዊ ዕድል እንዲያውም አይታሰብም” ይላሉ፡፡ (ሥነ ምግባር ገጽ ፶፫)

በአጠቃላይ የወጣትነት ጊዜ ለቀጣይ የዕድሜ ዘመናት መሠረት የሚጣልበት በመሆኑ በማስተዋል መጓዝን የሚጠይቅ ነው፡፡ ወጣቶች በዘመናቸው ልዩ ልዩ አካላዊ፣ ሥነ ልቡናዊ፣ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ተግዳሮቶች ሊገጥሟቸው ይችላል፡፡ ከእነዚህ ተግዳሮቶችም አንዱ ዘረኝት ነው፡፡

ዘረኝነት ምንድነው?

በማኅበራዊ ሳይንስ ዘርፍ ወጥነት ያለው ትርጕም ለመስጠት አስቸጋሪ ከሆኑ ቃላት አንዱ ዘር ወይም በእንግሊዝኛው (Race) የሚባለው ነው፡፡ በተለይም ዘር፣ ጎሳ፣ ነገድ፣ ብሔር ወዘተ የሚሉ ቃላት በተለያዩ አገራት የተለያየ ትርጕምና ይዘት ሊኖራቸው ስለሚችል ተመሳሳይ ግንዛቤ ለመያዝ አስቸጋሪ ያደርገዋል፡፡

ለአብነት አንዳንድ ሰዎች ከቅርብ ዐሥርት ዓመታት ወዲህ በሀገራችን የሚታየው የሕዝብ አለመረጋጋትና ቀውስ ምንጩ ተግባራዊ እየሆነ ያለው የኢትዮጵያ መንግሥታዊ አወቃቀር ዘርን ወይም ጎሳን ወይም ቋንቋን መሠረት ያደረገ በመሆኑ ነው ብለው ይሞግታሉ፡፡ ፖለቲከኞችም ይሁን የፖለቲካ ተንታኞች ይህን ይበሉ እንጂ አሁን ላይ ያለው የሃገሪቱ ሕገ መንግሥት መንግሥታዊ መዋቅሩ በዘር፣ ወይም በጎሳ፣ ወይም ደግሞ በቋንቋ ላይ የተመሠረተ ነው አይልም፡፡

የኢፌድሪ ሕገ መንግሥት አንቀጽ ፵፮ “ክልሎች የሚዋቀሩት በሕዝብ አሰፋፈር፣ ቋንቋ፣ የማንነት እና ፈቃድ ላይ በመመሥረት ነው” ይላል፡፡ ስለዚህ ከሕገ መንግሥት አንጻር ከተመለከትነው የሀገራችን ሕገ መንግሥት ለብቻው ነጥሎ በዘር፣ ወይም በቋንቋ፣ ወይም በጎሳ ላይ የተመሠረተ ነው እንደማይል አንብቦ መረዳት ይቻላል፡፡ ታዲያ መንግሥታዊ አወቃቀሩ በዘር ላይ ወይም በጎሳ ወይም በቋንቋ ላይ ነው የተመሠረተው የሚለው አባባል ምንጩ ምን ይሆን? ለሚለው መላምት ከመስጠት የዘለለ ተጨባጭ ማስረጃ ማግኘት አዳጋች ነው፡፡

እርግጥ አንዳንድ ፖለቲከኞችና የግል ጥቅማቸውን የሚያስቀድሙ ግለሰቦች ሕገ መንግሥቱን በራሳቸው አረዳድና ፍላጎት በመተረጎም ለራሳቸው ዓላማ ማስፈጸሚያ ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ኢትዮጵያውያን በቋንቋቸው፣ በባህላቸው፤ በሃይማኖታቸው በአጠቃላይ በማንነታቸው ምክንያት በደል ሊደርስባቸው ይችላል እንጂ የሀገራችን ሕገ መንግሥት ዘረኝነትን አያበረታታም፡፡ እንዲያውም “ማንኛውም ሰው በሕግ ፊት እኩል መሆኑንና ማንኛውም ሰው በዘር፣ በብሔር፣ በቀለም፣ በጾታ፣ በቋንቋ፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ፣ በማኅበራዊ አመጣጥ፣ በሀብት፣ በትውልድ ወይም በሌላ አቋም ምክንያት ልዩነት ሳይደረግ ሰዎች ሁሉ እኩልና ተጨባጭ የሕግ ዋስትና የማግኘት መብት አላቸው” ተብሎ በአንቀጽ ፳፭ በግልጽ ተቀምጧል፡፡ ስለዚህ ሕገ መንግሥቱ የሰው ልጅ እኩልነትን ያረጋግጣል፡፡ በዚህ ጉዳይ የሕግ ባለሙያዮች የበለጠ ማብራሪያ ሊሰጡበት ይችላሉ፡፡ በግርድፉ መረዳት የምንችለው ጉዳይ ቢኖር ግለሰቦችና ልዩ ልዩ የፖለቲካ ፍላጎት ያላቸው ቡድኖች ከሕግ በአፈነገጠ መንገድ በመጓዝ ሕዝብን ከሕዝብ የሚለያዩ አጀንዳዎችን በማቀበል አፍራሽ ተግባር ላይ መሠማራታቸውን ነው፡፡

በሕገ መንግሥቱ ላይ የተጠቀሰውና ምናልባትም የዘረኝነት ምንጭ ሊሆን ይችላል ተብሎ የሚገመተው “ማንነት” የሚለው ቃል ነው፡፡ ማንነት የሚለው ቃል ደግሞ የብዙ ጥቃቅን ማንነቶች ድምር ውጤት እንጂ በቀጥታ ዘርን ብቻ አያመለክትም፡፡ ለምሳሌ ጾታ ራሱን የቻለ ማንነት ነው፣ የቆዳ ቀለም አንድ ማንነት ነው፤ሃይማኖት አንድ ማንነት ነው፣ ኢትዮጵያዊነት አንድ ማንነት ነው፣ ቋንቋ አንድ ማንነት ነው፣ ወጣትነት ወይም ጎልማሳነት ወይም እርግና ሌላኛው ማንነት ነው፣ ወዘተ፡፡ እነዚህንና የመሳሰሉት ማንነቶች በአንድ ሰው ጥቅል ማንነት ላይ ሊኖሩ ይችላሉ ማለት ነው፡፡

የማኅበራዊ ሳይንስ አጥኚዎች ዘር የሚለውን ቃል በዋናነት ሁለት መገለጫዎች እንዳሉት ይናገራሉ፡፡ አንደኛው በግልጽ የሚታይና ከሌላው ማኅበረሰብ ሊለይ የሚችል የአካል ወይም የቆዳ ቀለም ልዩነት ሊኖር ይገባል ይላሉ፡፡ ለምሳሌ በምዕራቡ ዓለም የሰው ልጅ ጥቁርና ነጭ ተብሎ እንደሚከፋፈለው ዓይነት በግልጽ ሊታይ የሚችል አካላዊ መለያ ሊኖር ይገባል ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ የእገሌ ዘር አባል ነን ብለው ራሳቸውን ከሌላው ማኅበረሰብ አግልለው የራሳቸውን ማኅበረሰብ የፈጠሩና ከብዙኃኑ ማኅበረሰብ ራሳቸውን ያገለሉ ከሆነ ዘር የሚለውን መስፈርት ሊያሟሉ ይችላሉ ማለት ነው፡፡ ስለሆነም ዘር የማንነት አካል ሊሆን ይችላል እንጂ ማንነትን ሙሉ ለሙሉ ሊተካ አይችልም ማለት ነው፡፡

በአንጻሩ ጎሳ ማለት ሦስት መመዘኛዎችን የሚያሟላ ነው፡፡ የመጀመሪያው በአንድ ማኅበረሰብ ውስጥ የሚኖሩና የጋራ ማንነት ያላቸው ናቸው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ አንደኛውን ጎሳ ከሌላው ጎሳ የሚለዩበት ማንነት በዋናነት አካላዊ ገጽታ (Phisical appearance) ሳይሆን የጋራ የሚሉት ባህላቸው፣ ታሪካቸው፣ ቋንቋቸው ነው፡፡ ሦስተኛው መመዘኛ ደግሞ ከሌላው ማኅበረሰብ በተለየ ሁኔታ በቁጥራቸው ጥቂት(Minority) ስሜት ያላቸው ናቸው፡፡ በእኛ አገር ፖለቲከኞች ጎሳ የሚለውን ትርጓሜ ብሔር ወይም ብሔረሰቦች የሚለው ቃል ጥቅም ላይ ሲውል እንመለከታለን፡፡ ይህ ግን የተሳሳተ ትርጕም እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ፡፡

ስለ ማንነት፣ ስለ ዘር፣ እንዲሁም ስለ ጎሳ ይህን ካልን እገሌ ዘረኛ ነው፤ እገሊት ዘረኛ ናት፤ እነ እገሌ ዘረኞች ናቸው፣ በመካከላችን ዘረኝነት ተስፋፍቷል ወዘተ ስንል ምን ማለታችን ይሆን የሚለው መሠረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ እውነት በሀገራችን የምናስተውለው የእርስ በርስ መገፋፋት ጎሰኝነት የወለደው ነው ወይስ ዘረኝነት የወለደው የሚለው አነጋጋሪ ጉዳይ ነው፡፡ በእርግጥ አንዳንድ የማኅበራዊ ሳይንስ አጥኝዎች ዘረኝነትን ከአካላዊ ገጽታ ባሻገር ሰፋ አድርገው ይመለከቱታል፡፡

አንድን ግለሰብ ወይም ማኅበረሰብ ወይም ተቋም የሌላ ዘር ወይም ጎሳ አባል በመሆኑ ብቻ በማንነት ላይ የተመሠረተ ጭፍን፣ ጥላቻ፣ አድልዎ ወይም ጠላትነት ማለት ነው ይላሉ፡፡ ከዚህ አንጻር በሀገራችን የምንመለከተው ጭፍን ጥላቻ፣ አድልዎ ወይም ጠላትነት የአካል ገጽታን ወይም የዘር ሐረግን መሠረት ያደረገ ሳይሆን በዋናነት ባህልን፣ ቋንቋንና ሃማኖትን መሠረት ያደረገ ነው ብንል አሳማኝ ይሆናል፡፡

እዚህ ላይ አንድ እውነታን መረዳት የግድ ይለናል፡፡ ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው የሀገራችን ሕገ መንግሥት ለማንነት ትልቅ ቦታ ይሰጣል፡፡ ለሰው ልጅ እኩልነትም ትልቅ ቦታ ይሰጣል፡፡ ነገር ግን በማንነት ላይ የተመሠረተ መንግሥታዊ አስተዳደር በባሕርዩ አግላይ በመሆኑ በሕዝቦች መካከል አለመግባባትና ግጭት እንዲፈጠር ዕድል ይፈጥራል፡፡ ምንም እንኳ በሕግ ደረጃ የተቀመጠ አግላይነት ባይኖርም በመንግሥት መዋቅር ላይ የተቀመጡ አንዳንድ ፖለቲከኞች የእኔ ለሚሉት ግለሰብ ወይም ማኅበረሰብ ሊያደሉ ይችላሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አስተዳደር በሕዝቦች መካከል ማንነትን መሠረት ያደረገ ጭፍን ጥላቻና አግላይነት ሊፈጥር ይችላል፡፡ አሁን ላይ በአገራችን እየተስተዋለ ያለው የዜጎች መፈናቀል፣ ስደትና ሞት በዋናነት በማንነት ላይ የተመሠረተ ጭፍን ጥላቻና አግላይነት የወለደው እንደሆነ እሙን ነው፡፡

ይቆየን፡፡

የቴክኖሎጂ ጥቅም በኦርቶዶክሳዊ ክርስትና እይታ

በዲ/ን በረከት አዝመራው

የሰው ልጆች በምድራውያኑ ፍጥረታት ውስጥ ካሉት ድርሻዎች ውስጥ መሪነት እና ገዢነት ይጠቀሳሉ፡፡ “ምድርን ሙሏት … ግዟትም” የሚለው ቃል ለሰው ልጅ የተሰጠውን ኃይል፣ ዕውቀትና ሥልጣን የሚገልጥ ነው፡፡ (ዘፍ. ፩፥፳፰)፡፡ ይህ ገዢነትና በእነዚህ ፍጥረታት ላይ የተሰጠው ሥልጣን በምን ገለጣል? ሰው ይህን ለማድረግ የሚያበቃ ምን ነገር አለው? እንዲገዛቸውና እንዲጠቀምባቸው ከተፈጠሩት ፍጥረታት መካከል ከእርሱ የሚበረቱ፣ የሚፈጥኑ እና የሚገዝፉ ፍጥረታት እንዴት ከበታቹ ሊሆኑ ይችላሉ? የሚል ጥያቄ ልናነሣ እንችላለን፡፡

ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ የምናገኘው የሰውን ጥንት ተፈጥሮ በማስተዋል ነው፡፡ ሰውን ይህን ክብር ያቀዳጀው የሰው በእግዚአብሔር አርአያና አምሳል መፈጠሩ ነው፡፡ (ዘፍ. ፩፥፳፮-፳፯)፡፡ ሰው በእግዚአብሔር አርአያ እና አምሳል ተፈጠረ ስንል የእግዚአብሔር የባሕርይው መገለጫዎች ወሰን የሌላቸው እና ከማንም ያልተቀበላቸው ናቸው፤ ባሕርይውን ደግሞ ለሰው ልጅ በፀጋ ሰጥቶታል ለማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር በባሕርይው አዋቂ እንደሆነ ሁሉ ሰውም የፀጋ አዋቂነት ተሰጥቶታል፤ እግዚአብሔር በባሕርይው ገዥ(ንጉሥ) እንደሆነ ሁሉ ለሰውም በፀጋ በምድራዊው ሁሉ ገዥነት ተሰጥቶታል፡፡ እግዚአብሔር የባሕርይ አምላክ በመሆኑ ሁሉም ፍጥረታት በፍርሃት እና በአክብሮት ሆነው በፊቱ እንደሚቆሙ ሁሉ ሰውም እግዚአብሔር ከሰጠው የፀጋ አምላክነት እና ግርማ የተነሣ በኃጢአት ከመጎስቆሉ በፊት ምድራውያን ፍጥረታት በአክብሮትና በፍርሃት ይታዘዙት ነበር፡፡ ይህም የሚታወቀው አስፈሪ የሆኑ አራዊት እንኳን ሳይቀሩ ለቅዱሳን በሚያሳዩት አክብሮትና መታዘዝ ነው(ዘፍ. ፪፥፳)፡፡

ለሰው ልጅ ከእግዚአብሔር የተሰጠው ዕወቀት፣ ጥበብ እና ማስተዋል አለው፡፡ ሰው ቢበድለውም እንኳን የሰጠውን ዕውቀት፣ ጥበብ እና ማስተዋል አለመግፈፉ ከቸርነቱ የተነሣ ነውና ይህ የእግዚአብሔርን ቸርነት፣ ለሰው ያለውን ርኅራኄ እና መግቦት ያሳያል፡፡ በዓለማችን በዘመናት የምናያቸው ዕውቀቶች፣ ጥበቦች እና በማስተዋል የተገኙ ግኝቶች ሁሉ ከዚህ ከእግዚአብሔር ሥጦታ ምንጭ እንደ ወንዝ የሚፈሱ የፀጋ ሥጦታዎች ናቸው፡፡

በዘመናችን ተስፋፍትው የምናያቸው የሳይንስና የቴክኖሎጂ ግኝቶችም የዚሁ አካል ናቸው፡፡ የሰው ልጅ ይህ በተፈጥሮ የተሰጠውን አዋቂነት እና ጥበብ ተጠቅሞ በየዘመኑ ሕይወቱን ያሳልጥበታል፤ የየዘመኑን ፈተናዎች ይቋቋምበታል፤ በአጠቃላይ ሕይወቱን በአግባቡ ለመምራት ይጠቀምበታል፡፡

ጠለቅ ብለን ስናየው የሳይንስና የቴክኖሎጂ ዕድገት እግዚአብሔር በሰው ውስጥ ያስቀመጠው መግቦት ነው፡፡ ይህን በጥንት ተፈጥሮ የሰጠውን ፀጋ በበደለው ጊዜ እንኳን አልነሳውም፤ ይህም ከላይ እንዳልነው የቸርነቱ ውጤት ነው፡፡

ልዑል እግዚአብሔር ለሰው የመግቦት አካል ይሆን ዘንድ፣ በኑሮው የሕይወቱን ውጣ ውረድ እንዲያቀልለት ዕውቀትንና ጥበብን በመስጠቱ ሰው በአእምሮው የዕውቀት ምጥቀትና በጥበቡ እየታገዘ እግዚአብሔር የፈጠራቸውን ፍጥረታት በመጠቀም ብዙ ድንቅ የሆኑ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን አስገኝቷል፡፡ ይህ መልካም ነገር ነው፤ እግዚአብሔርንም የምናመሰግንበት አንድ ትልቅ ምክንያትም ነው፡፡ በመልካም ልቡና ስናስተውለው የእግዚአብሔርን ቸርነት እና ኃያልነት የምናስብበት ሥጦታ ነው! የፈጠረው ሰው ይህን ያህል ጥበብና ኃይል እንዲኖረው ያደረገ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡

ነገር ግን ቴክኖሎጂ መልካም የሚሆነው ለመልካም ነገር ስንጠቀምበት ነው፡፡ ዕውቀቱንና ማስተዋሉ ሲሰጠን ለመልካም እንድንጠቀምበት ቢሆንም ለክፉም ልንጠቀምበት እንችላለን፡፡ ይህም ከነፃ ፈቃድ የተነሣ ነው፤ እግዚአብሔር ለሰው የሰጠው ዕውቀትን ብቻ ሳይሆን ወደ ፈለገው የሚሄድበትን ነጻ ፈቃድም ጭምር ነውና፤ ለመልካም ብንጠቀምበት እግዚአብሔርንም ሰውንም እናስደስታለን፤ ለበለጠ ሰማያዊ እና ዘለዓለማዊ ዕወቅትም የተገባን ሆነን እንገኛለን፡፡ ለኃጢአት ብንጠቀምበት ግን እንኳን የሠራነው ቴክኖሎጂ ቀርቶ የገዛ ሰውነቶቻችንም ይረክሳሉ፤ ከሰማያዊው ርስት ዕድል ፈንታ አይኖረንም፡፡ ስለዚህ ቴክኖሎጂ በመልካም ኅሊና ሊመራ ይገባዋል ማለት ነው፡፡

አሁን የምናየው የቴክኖሎጂ ዕድገት የሚመራው በምን ኅሊና ነው? ይህ በተለይ በክርስቲያኖች ዘንድ ሊስተዋል የሚገባው ጠቃሚ ጥያቄ ነው፡፡ ቴክኖሎጂን የሚመራው የሰው ኅሊና ለመልካምነቱ ወሳኝ ነው፤ ኅሊና ጤናማ ከሆነ ቴክኖሎጂም ጤናማ አገልግሎት ይሰጣል፤ ካልሆነ ግን ወደ ሞት ይዞን ሊወርድ ይችላል፡፡

ይህን የተክኖሎጂ ጤነኛነት ቢያንስ በሁለት መንገድ ልንመዝነው እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው ለስንፍና፣ ለኃጢአት፣ ለትዕቢት እና ለአምባገነንነት መሣሪያ ከሆነ ጤናማ አይደለም፡፡ ሰው ቴክኖሎጂን ተጠቅሞ ኃጢአት የሚሠራ እና ሌሎችን የሚበድል ከሆነ ለራሱ መጥፊያ እየተጠቀመበት ነው ማለት ነው፡፡ በቴክኖሎጂ ብዛት የማይዳንባት የእግዚአብሔር ፍርዱም የኋለ ኋላ ታጠፋዋለች፡፡

ሁለተኛው ችግር ደግሞ ቴክኖሎጂን ከመጠን በላይ ቦታ ሰጥቶ እንደ አምላክ ማየት ነው፡፡ የሕይወት መጨረሻ መንግሥተ ሰማዯትን ወርሶ ከእግዚአብሔር ጋር መኖር እንጂ ቴክኖሎጂን እንደ ምኞት መዳረሻ ቆጥሮ በዚህ ምኞት ውስጥ ራስን አስክሮ መኖር አይደለም፡፡ “በሰለጠነው ዓለም” ሰዎች ለራሳቸው ለፈጠሯቸው ለሳይንስና ለቴክኖሎጂ ሥራዎች ለፈጣሪ የሚሰጠውን ዓይነት አክብሮትና ምስጋና ሲቸሯቸው እናስተውላለን፡፡ ቴክኖሎጂ ጣዖታችን ከሆነ መሞቻችን ሆኗል ማለት ነው፡፡

እኛ ክርስቲያኖች ግን ቴክኖሎጂን መጠቀም ያለብን የምኞታችን ሁሉ መዳረሻ አድርገን ሳይሆን በዚህ ምድር ለምንኖረው ኑሮ ለመልካም ሥራ መሣሪያ እንዲሆነን እንጂ በራሱ ግብ ስለሆነ አይደለም፡፡

ይህች ዓለም በቴክኖሎጂ ሳይሆን በእግዚአብሔር ኃይል እና መግቦት እንደምትኖር ያለ ግብዝነት ልናምን ይገባል፡፡ ቴክኖሎጂ ራሱ እግዚአብሔር ለሰው ከሰጠው ዕውቀት የተነሣ እንደሆነና በአግባቡ ከተጠቀምንበት ለመልካም ነገር መሣሪያ የሚሆን የሰው ልጅ ሀብት እንደሆነ ሁል ጊዜ ማሰብ ማሰላሰል ይኖርብናል፡፡ ካልሆነ ግን መልካም ሥጦታነቱ ቀርቶ ለሰው ልጅ የከንቱነት ምክንያት እንዲሁም ለጥፋቱ መሣሪያ ሊሆን እንደሚችል እናውቃለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን አጠቃቀም

መ/ር በትረ ማርያም

ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን እውነተኛና ሐሰተኛ መረጃዎችን በጽሑፍ፣ በድምጽ፣ በምስል ወድምጽና በመሳሰሉት መንገዶች ለሕዝብ የሚሰራጭበት የመገናኛ ዘዴ ነው። ሆኖም አንድ ሰው ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ሲጠቀም በሐሰቱ እንዳይጎዳ፣ በእውነቱ እንዲጠቀም እውነቱን ከሐሰት የሚለይበት ማንጸሪያ ወይም መመዘኛ ሊኖረው ያስፈልጋል፡፡ የተጻፈ ወይም የተነገረና የታየ ሁሉ እውነት አይደለምና።

የሰው ልጅ ለተለያየ ዓላማ አንድን ሐሳብ በፈለገው መንገድ ሊገልጽ ይችላል፡፡ ነገር ግን የገለጸበት መንገድና ሁኔታ ምን ዓይነት መረጃ፣ ለማን፣ እንዴት፣ ወዘተ ለሚሉት ጥያቄዎች በተገቢው መንገድ ምላሽ የሚሰጥ መሆን ይገባዋል፡፡ መረጃውም ሊጠቅምና ሊጎዳ እንደሚችል በቅድሚያ መረዳት ይገባል፡፡ እውነትን ቢናገር እንኳ የተናገረው ምን አስቦ ወይም ለምን ዓላማ እንደሆነ ስለማናውቅ የመታለል ዕድላችን ከፍ ያለ ሊሆን ይችላል።

ስለዚህ በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የሚለቀቁ መረጃዎች ትክክለኛ ከሆኑ አዎንታዊ ተጽእኖ በሐሰት የተሞሉ ከሆኑ ደግሞ አሉታዊ ተጽእኖ በማኅበረሰቡ ላይ የማሳደር አቅማቸው ከፍተኛ ነው፡፡ በዚህም መሠረት በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የተጻፉ ጽሑፎችን፣ የተለጠፉ የምስል ወድምጽ መልእክቶችን ስናይ ስለ ማንነታቸውና ስለ ውጤታቸው አዎንታዊነትና አሉታዊነት ለመረዳት መጠየቅ ያለብን ጥያቄዎች አሉ። ጥቂቶቹን ብንመለከት፡-

 . መልእክቱ ምንድን ነው?፡- በማኅበራዊ የመገናኛ ብዙኃን የተላለፈው ጉዳይ መልእክት ምንነት እና ፍሬ ነገር ምንድን ነው? የሚለውን መጠየቅ ያስፈልጋል። ዝም ብለን የጉዳዩን ምንነት ሳንረዳ ሌሎች ስላራገቡት የምንቀበለው መሆን የለበትም። በተአምረ ኢየሱስ የተጻፈ አንድ ታሪክ አለ።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ አብነት ለመሆን ትምህርት ይማር ዘንድ ወደ መምህር ሄደ። (አስተውል ለመምህሩ ዕውቀትን የሰጠ ጌታ ለእኛ አብነት ለመሆን ሲል ሄደ እንጂ አዲስ ዕውቀት ለመገብየት አይደለም)። ከዚያ መምህሩ ፊደል ሊያስተምረው “አሌፍ” በል አለው። ጌታም “አሌፍ” አለ። ከአሌፍ ቀጥሎ ያለው ፊደል “ቤት” ነውና “ቤት” በል አለው።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን መጀመሪያ የአሌፍ ትርጉሙ ምንድን ነው? የዚህን ምሥጢር ንገረኝና ቀጣዩን እለዋለሁ ብሎታል። ስለዚህ እኛም ጉዳዩን በቅርበት በስሜት ሕዋሳቶቻችን ዳስሰን፣ ዐይተንና ቀምሰን ያላረጋገጥነውን ጉዳይ ወይም በሃይማኖት ትምህርት ያልተማርነውን ጉዳይ የሆነ አካል ጽፎት ብናገኝ ስለተጻፈው ጽሑፍ ምንነት የጻፈውን አካል ጠይቀን ወይም በሌላ መንገድ መረዳት ይጠበቅብናል፡፡ ይህም የመልእክቱን ምንነት መለየትና መገንዘብ ያስችለናል፡፡

. ማን ጻፈው?፡- ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ “ይደልዎ ለዘያነብብ ቅድመ ይዝክር ስሞ ለበዓለ መጽሐፍ ወእምዝ ያንብብ ወይምሀር፤ የተጻፈን ነገር ለሚያነብ ሰው የተጻፈውን ጉዳይ ከማንበቡ በፊት የጸሓፊውን ማንነት ይወቅ፣ ካወቀ በኋላ አንብቦ ያነበበውን ያስተምር” ይላል። የጸሓፊውን ማንነት ማወቅ የጽሑፉን ስሜት እንድንረዳው ይረዳናል። ከዚያም ጽሑፉን አንብቦ የተጻፈበትን ዐውድ ተረድቶ ምን ለማለት እንደፈለገ በቀላሉ መረዳት ያስችላል፡፡ ክርስቶስን ሐዋርያት ብቻ ሳይሆኑ ብዙ ሰዎችም ተከትለውት ነበር። ነገር ግን የሚከተለው ሕዝብ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የነበረው አመለካከት የተለያየ ነበር። “መጥምቁ ዮሐንስ ነው የሚሉ አሉ፤ ሌሎችም ኤልያስ፣ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ፡፡”(ማቴ.፲፮፥፲፬)፡፡ አስተውል የሚከተሉትን ሰው ማንነት አለማወቅ ከትልቅ ክሕደት ውስጥ ይከታል። ፈጣሪያቸውን እንደ ፍጡር አቅርበውት ነበር። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ ቢላቸው ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” ብሎ ቢመልስ “አንተ ብፁዕ ነህ” ተብሎ ክብር ተሰጥቶታል።

በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ባለቤታቸው የማይታወቁ ብዙ ጽሑፎች እና የድምጽ እንዲሁም የምስል ወድምጽ መረጃዎች ይለቀቃሉ። በዚህን ጊዜ በአእምሯችን የሚጭኗቸው መልእክቶች ይኖሯቸዋል። ስለዚህ መልእክቱ ከእውነተኛነቱ አልፎ ክርስቲያናዊ ወይም ኦርቶዶክሳዊ ነው ወይ? የሚለውን መመዘን ያስፈልጋል። ስለዚህ ማኅበራዊ መገኛ ብዙኃን ስንጠቀም መምረጥ አለብን ማለት ነው።

. የት ተጻፈ?፡- ድርጊቱ የተፈጸመው የት ነው? የሚለው መታወቅ አለበት። በውጭ ሀገር የተደረገውን ድርጊት በሀገራችን እንደተደረገ እያደረጉ እያቀረቡ ሰውን ስሜታዊ የሚያደርጉ፣ ዋሽተው የሚያስዋሹ ብዙ ሰዎች አሉ። ስለዚህ የሆነን ድርጊት ወይም ጉዳይ አምነን ከመቀበላችን በፊት በተለያየ መንገድ ትክክለኛነቱን ማረጋገጥ ይገባል። ለማረጋገጥ በቂ ማስረጃ ካላገኘን ጉዳዩን ለሌሎች ከማካፈል መቆጠብ፣ እኛም ከመደናገጥና ከስሜታዊነት ርቀን በሰከነ መንገድ ልንጓዝ ያስፈልጋል፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ የሶስናን ታሪክ ሙሉውን ስናነብ የምናስተውለው አንድ ነገር አለ። ረበናት ከሶስና ጋር መተኛት ይፈልጋሉ። እርሷ ግን እምቢ ትላቸዋለች። በዚህ ምክንያት በሐሰት ይከሷታል። የሚመለከታቸው አካላትም ጉዳዩን ሳይመረምሩ ሶስናን ለመግደል ይዘጋጃሉ። ዳንኤል ግን ጉዳዩን እንመርምረው ብሎ የት አገኛችኋት ብሎ ሲጠይቃቸው ከተለያየ ቦታ ተናገሩ። በዚህ ጊዜ ውሸታቸው ታውቋል። ስለዚህ እኛም በውሸት እንዳንታለል “የት?” ብለን መጠየቅ አለብን።

. መቼ ተጻፈ? የሰማነው ወይም ያየነው ነገር መቼ የተፈጸመ ነው? የሚለውን ማወቅ ያስፈልጋል። ምክንያቱም ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ከዓመታት በፊት የተደረገውን ጉዳይ ዛሬ እንደተደረገ አድርገው ከዚህ ቀደም ያላየውን ሰው ያታልሉበታል። ከውጭ ሀገርም ይሁን በሀገር ውስጥ ከዓመታት በፊት የተቃጠለውን ቤት፣ የሞተውን ሰው ዛሬ የተደረገ አስመስለው ሰውን ከሰው ያጣሉበታል። ስለዚህ የምንሰማውን ነገር መቼ እንደተደረገ ማወቅ ያስፈልጋል። ጌታችን ሐዋርያትን በደብረ ዘይት ሰብስቦ ስለ ዳግም ምጽአት እና ምልክቶቹ ሲነግራቸው ይህ መቼ ይሆናል? ብለው ጠይቀውታል። (ማቴ. ፳፬፥፫) እኛም መረጃን ለማጣራት መቼ ብለን መጠየቅ አለብን። አለበለዚያ ግን ተሳስተን ልናሳስት የተሳሳተ መረጃ አጋርተን እኛንም ሌላውንም ልንጎዳበት እንችላለንና መጠንቀቅ አለብን።

. ስንት?፡- ብዙ ጊዜ አንዱ የሠራውን በደል ብዙ ሰው እንደሠራው አድርጎ ማቅረብ እና ብዙ ሰው የሠራውን አንድ ሰው ወይም ጥቂት ግለሰቦች እንደሠሩት አድርጎ መረጃ ሊለቀቅ ይችላል።

ለምሳሌ በአንዱ ሰው ወንጀል ያ ሰው የተወለደበትን ሰፈር ወይም ብሔር መስደብ ትልቅ ችግር ሊያስከትል የሚችል ነው። ተጠያቂም መሆን ካለበት ራሱ ተናጋሪው አካል ወይም ቡድን እንጂ በጅምላ የተወለዱበትን ቦታ መስደብ ትልቅ በደል ነው። ምናልባት ወንጀል ፈጻሚው ሰው በሥነ ምግባሩ ምክንያት ሕዝቡ የናቀው ሊሆን ይችላል። ስለዚህ አንድን ጉዳይ ዝም ብለን ከመቀበላችን በፊት ስንት ሰው አደረገው? የሚለውን መረጃ ጠይቀን ማወቅ ይጠበቅብናል ማለት ነው። ስንት የቦታን ስፋት፣ የጊዜን መጠን፣ የሰውን ብዛት ሊያሳውቀን ይችላልና። ብዙዎች የሠሩትን ወንጀል አንድ ሰው እንደሠራው አድርጎ ማቅረብም ሊኖር ይችላል።

፮. እንዴት?፡- በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የሚለቀቁ  አንዳንድ መልእክቶች ደግሞ ከነባራዊው እና ከተፈጥሯዊው ጉዳይ ያፈነገጡ ሊሆኑ ይችላሉ። ዝም ብለን የምንቀበላቸው አይደሉም። እኛ ከለመድነው እንዲሁም ከተማርነው እና ካየነው የተለየ ነገር ሲነገር እና ሲተላለፍ እንዴት? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል።

፯. ለምን?፡- በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ብዙ መረጃዎች በተለያየ መንገድ ይለቀቃሉ። መልእክቶቹን የሚለቀው ሰው ግን ምክንያት አለው። እውነቱንም ይሁን ሐሰቱን መረጃው ለሚደርሳቸው አካላት ማሥረፅ የፈለገው ጉዳይ አለው። ስለዚህ አንድን መልእክት በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ተጽፎ ስናገኘው ቀጥታ በእኛ አረዳድ ብቻ ሳይሆን በጸሓፊው አረዳድ ልንረዳው ይገባል። መልእክቱን ዐይተን ቀጥታ ማመን የለብንም። ለምን ብለን መጠየቅ አለብን። አንድ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ በተማሪዎች የሚነገር ቀልድ (ተረት) አለ። በአንድ ወቅት ምሽት ላይ አንድ የተማሪዎች ማደሪያ ክፍል መቃጠል ይጀምራል። ከዚያ ተኝተው የነበሩ ተማሪዎች ይነቁና ማደሪያ ክፍላቸው እየተቃጠለ መሆኑን ሲያውቁ ራሳቸውን ለማትረፍ ተደናግጠው ራቁታቸውን እየሮጡ ይወጣሉ፡፡ ከዚያ ቤተ መጻሕፍት ቆይቶ የመጣ ተማሪ ወደ ቤቱ ሲመለስ ብዙ ሰው ራቁቱን እየሮጠ ያያል። ይህን ጊዜ እርሱም ልብሱን አውልቆ ተከተላቸው ይባላል። አሁን ይህ ሰው ያለ ምክንያት የሚንቀሳቀስ ሰው ነው። እነርሱስ ከምንቃጠል ብለው ለማምለጥ በደመ ነፍስ ያደረጉት ነው። እርሱ ግን ዝም ብሎ እነርሱን ብቻ ዐይቶ ምክንያቱን ሳይረዳ አውልቆ ተከትሏቸዋል። እኛም በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የሆነ ታወቂ ሰው ወይም የማኅበራዊ አንቂ(Activist) ግለሰብ ስለጻፈው እሱን ተከትለን የምናስተጋባና ለሌሎች የምናጋራ መሆን የለብንም።

ግለሰቡ ለሆነ ዓላማ ውሸቱንም ይሁን እውነቱን መረጃውን ሲያዘጋጀው የሚያስከትለውን ችግር ተረድቶም ሆን ሳይረዳ ወይም ሆነ ብሎም ሲያደርገው ተከፍሎት ሊሆን ይችላል። ከዚህ በተጨማሪም ከየት ወደ የት፣ ከምን፣ በምን፣ እስከምን…. ወዘተ” እያልን ነገርን አጥርተን ለነፍሳችንም ለሥጋችንም የሚጠቅመንን መረጃ ልንይዝ ይገባናል።

ከላይ እንደተገለጸው መረጃ ስላገኘን ብቻ የሚያስከትለውን ችግር ሳንረዳ በማኅበራዊ ሚዲያ መልቀቅ በርካታ ችግሮችን በግለሰቦች፣ በቤተሰብ፣ በአካባቢና ብሎም በሀገር ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ጉዳት ከግንዛቤ በማስገባት መዝነን መጠቀም አስፈላጊ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ የምንጠቀምበት ሰዓትም ገደብ ሊኖረው ይገባል። ቀኑን ሙሉ ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ላይ ተጠምዶ መዋልና መከታተል ሱስ እንዳይሆንብንም መጠንቀቅ አለብን።

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።

አስተርእዮ​ ​ማርያም

አስተርእዮ ማለት መታየት፣ መገለጥ ማለት ነው። ቃሉ አስተርአየ ታየ፣ ተገለጠ ከሚለው የግዕዝ ግሥ የተገኘ ነው። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገባው ቃል ኪዳን መሠረት በሥጋ የተገለጠበት(የታየበት)፣ አንድነት ሦስትነቱም የተገለጠበት ወቅት በመሆኑ ከልደት በዓል እስከ ጥር መጨረሻ በሙሉ ዘመነ አስተርእዮ በመባል ይታወቃል። የእመቤታችን በዓለ ዕረፍት በዘመነ አስተርእዮ ውስጥ ስለሚከበር “አስተርእዮ ማርያም” ተብሏል።

ልቡናዋ በይኩነኒ የጸና ንጽሐ ሥጋ፣ ንጽሐ ነፍስ፣ ንጽሐ ልቡና አስተባብራ የያዘች ወላዲተ አምላክ ምንም እንኳን የአምላክ እናት ብትሆንም ሞተ ሥጋ ለሁሉም ዕጣ ፈንታ በመሆኑ በቃል መነገሩ በልብ መታሰቡ ከፍ ከፍ ይበልና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ተንሥኢ ወንዒ፤  የነፍሴ ደስታ የኾንሽ ውድ እናቴ ሆይ ተነሥተሽ ወደ እኔ ነዪ” (መኃ ፪፥፲) ብሏታል።

ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኲሉ

ቅዱስ ዳዊት ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ሀገረ እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር ማኅፀንሽን ከተማ አድርጎ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን የኖረብሽ ሆይ ስለ አንቺ የተነገረው የተደረገው ነገር ዕጹብ ድንቅ ነው እንዳለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ እናት ሆና ማረፏ ይደንቃል። ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ ሞቷ የሚያስደንቅ መሆኑን “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኲሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው ሁሉ የተገባ ነው የማርያም ሞት ግን ሁሉን ያስደንቃል” በማለት ገልጾታል።

ሞት በጥር ነሐሴ መቃብር

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሞትና ትንሣኤ በነገረ ማርያም አበው እንደሚያስረዱት ዕረፍቷ በጥር ፳፩ እሑድ ነው። አባቶቻችን በጾመ ፍልሰታ ውዳሴ ማርያም ቅዳሴ ማርያም ሲተረጉሙ የእረፍቷን ነገር እንዲህ ብለው ይተርካሉ።

የእረፍቷስ ነገር እንደምን ነው ቢሉ ስድሣ አራት ዓመት በዚህ ዓለም ኖራ ጥር ፳፩ በእሑድ ቀን ጌታ እልፍ አዕላፋት መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ እናቴ ሆይ ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍሽ መጣሁ አላት። ልጄ ሰማይና ምድር የማይወስኑህ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኔ ተሸክሜ በድንግልና ወልጄህ እሞታለሁን? አለችው። በሲዖል የሚሰቃዩ ነፍሳትን አሳይቶ እናቴ ሆይ ሞትሽ ለእነዚህ ቤዛ ይሆንላቸዋል አላት። እሊህን ከማርክልኝስ ይሁን አለችው። ቅድስት ሥጋዋን ከቅዱስ ነፍሷ ለይቶ በቃለ አቅርንት በዝማሬ መላእክት አሳረጋት። ደቀ መዛሙርቱንም ከያሉበት በደመና ጠቅሶ ካለችበት አድርሶ እመቤታችሁን ሥጋዋን በክብር አሳርፉ አላቸው። ሐዋርያት በአጎበር አድርገው ወደ ጌቴሰማኒ ይዘው ሲሄዱ አይሁድ ቀድሞ ልጇን ተነሣ ዐረገ እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ አሁን ደግሞ እሷን ተነሣች ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን በእሳት እናቃጥላታለን ብለው ተነሡ። ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው። መልአክ መጥቶ በሰይፍ ሁለት እጁን ቀጣው ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ። በድያለሁ ማሪኝ ብሎ ቢማጸናት እጁ ተመልሶለታል። ከዚህ በኋላ ዮሐንስን ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት አግብቶ ከዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት።

ቅዱስ ዮሐንስን እንደምን ሆነች አሉት ከገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች አላቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አይቶ እኛ ሳናይ ብለው በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፡፡ ሁለት ሱባዔ ሲፈጸምም እሑድ አምጥቶ ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፡፡ በሶስተኛው ቀን ማክሰኞ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ተነሥታለች።” ቅዱስ ቶማስ አልነበረምና ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ ዛሬም ደግሞ ያንችን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን ብሎ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ፤ ከሐዘኑ የተነሣ ሊወድቅ ወደደ” እመቤታችንም አይዞህ አትዘን እሊያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም አንተ አይተሃል ተነሣች ዐረገች ብለህ ንገራቸው ብላ የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው። ከዚህ በኋላ ሂዶ የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ አላቸው አግኝተን ቀበርናት አሉት ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተው ይህ ነገር አይመስለኝም አላቸው። ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ ልማድህ ነው አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራልህ ብሎ ተቆጥቶ ወደ መቃብሩ ሂዶ ቢከፍተው አጣት፤ ደንግጦ ቆመ ሐዋርያው ቶማስም አታምኑኝም ብዬ እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች አላቸው፤ የያዘውንም ሰበን ሰጣቸው፤ ለበረከትም ተካፍለውታል። በዓመቱ ሐዋርያት ቅዱስ ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ ብለው ጾም ጀመሩ በ፲፮ኛው ቀን እመቤታችንን መንበር አድርጎ ቅዱስ ጴጥሮስን ካህን ዘይትራድኦ ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ በዚያው ላይ ቀድሶ አቁርቧቸዋል። ቤተ ክርስቲያንም ይህንን መታሰቢያ አድርጋ በየዓመቱ ታከብረዋለች።

ሰአሊ ለነ ቅድስት

የኃጥአንን ለቅሶና ሐዘን አይተሽ ስለ እነርሱ ድኅነት(መዳን) ዕረፍትሽን በሀሴት የተቀበልሽ እመቤታችን ሆይ ሐዋርያት በሱባዔ ትንሣዔሽን ለማየት በቅተዋልና እኛም በዓለ ዕረፍትሽን አክብረን ልጅሽ በሰጠሽ ቃል ኪዳን በቀኙ እንቆም ዘንድ ለምኝልን። አሜን።

ምንጭ፡- በኢት/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጅ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ

በዓለ ጥምቀት

ጥምቀት አጥመቀ፤ አጠመቀ (ነከረ)፣ ውኃ ውስጥ ገብቶ መውጣት፣ መዘፈቅ፣ መጥለቅ ማለት ነው፡፡ ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የመጀመሪያውና የሌሎች ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን መግቢ በር ነው፡፡ በቁስጥንጥንያ የተሰበሰቡ መቶ ሃምሳው አባቶች “ወነአምን በአሐቲ ጥምቀት፤ በአንዲት ጥምቀት እናምናለን” በማለት እንደመሰከሩት፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥምቀት በዓልን ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት  ቀጥላ ከቅጽረ  ቤተ ክርስቲያን ወጥታ  በዱር፣ በሜዳ፣  በወንዝ፣ በባሕር  ዳርቻ  ጥር ፲፩  ቀን  በየዓመቱ  በታላቅ ድምቀት የምታከብረው በዓል ነው፡፡

ጥምቀት ሰው በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቆ የእግዚአብሔር ልጅ የሚሆንበት ታላቅ ምሥጢር ነው (ማቴ፣ ፳፰፥፲፰)፡፡ ይህ ምሥጢር ከምሥጢራት ሁሉ የመጀመሪያ ነው። ምሥጢር መባሉም በዓይን በሚታይና በጆሮ በሚሰማ አገልግሎት በዓይነ ሥጋ የማይታይና በዕዝነ ሥጋ የማይሰማ ጸጋ ስለሚገኝበት ነው። አገልግሎቱ ሲፈጸም ይታያል፣ ይሰማል፤ ተጠማቂው ከውኃና ከመንፈስ ተወልዶ የልጅነት ጸጋ ሲያገኝ ግን አይታይም፣ አይሰማም። ይህ ምሥጢር የሌሎች ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንና የመንግሥተ ሰማያት መግቢያ በር ነው። ይኸውም ይታወቅ ዘንድ ጌታችን በወንጌል “ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም” ብሏል (ዮሐ. ፫፥፯)፡፡ ይህንን ነው ጌታችን ዳግም ልደት ያለው (ዮሐ. ፫፥፫)፡፡ የመጀመሪያው ልደት ከአባት አብራክና፣ ከእናት ማኅፀን በሥጋ መወለድ ሲሆን ሁለተኛው ልደት ግን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና፣ ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ረቂቅ በሆነ ልደት በመንፈስ መወለድ ነው። ይህንንም ጌታችን “ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፤ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው” ብሎታል (ዮሐ. ፫፥፮)፡፡

ጥምቀት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሚከበረው በየዓመቱ ጥር ፲፩ ቀን ነው። በጥምቀት በዓል የታቦታቱ ወደ ወንዝ መውረድ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  በእደ ዮሐንስ ለመጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ የመሄዱ ምሳሌ ነው። በዮርዳኖስ የተጠመቀውም ስለ ሁለት ነገር ነው፦

፩ኛ• ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ባሕር አየች ሸሸችም፤ ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ” ብሎ የተናገረውን ትንቢት በእርሱ ጥምቀት ለመፈጸም( መዝ፣፻፲፫፥፫)፡፡

፪ኛ• በዮርዳኖስ ተጥሎ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤያችንን እንደ ሰውነቱ ረግጦ፤ እንደ አምላክነቱ አቅልጦ ሊደመስስልን።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ በሠላሳ ዓመቱ ለድኅነተ ዓለም፣ አንድም ለአብነት በፈለገ ዮርዳኖስ በዮሐንስ ወልደ ዘካርያስ ተጠምቋል። በተጠመቀ ጊዜም የባሕርይ አባቱ አብ በደመና ሆኖ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው” ብሎ መስክሯል፤ መንፈስ ቅዱስም በፀአዳ ርግብ አምሳል በራሱ ላይ ተቀምጧል። (ማቴ. ፫፥ ፲፫–፲፯)፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ መጠመቁን ምክንያት በማድረግ ለዚህ ቅዱስ ዕለት በዓል ሠርታ ታከብረዋለች፡፡ በየዓመቱም ታቦታቱ በዋዜማው ከየአብያተ ክርስቲያናቱ ወጥተው በአደባባይ በሊቃውንቱ እና በሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች እንዲሁም በምእመናን በዝማሬ ታጅበው ወደ ጥምቀተ ባሕር በመውረድ በወንዝ ዳር ወይም  በሰው ሠራሽ የውሃ ግድብ አጠገብ በዳስ ወይም በድንኳን ያድራሉ። ሌሊቱንም በማኅሌትና በቅዳሴ ስብሐተ እግዚአብሔር ሲደርስ አድሮ ሥርዓተ ቅዳሴው ይፈጸማል። ሲነጋም በወንዙ ዳር ጸሎተ አኰቴት ተደርሶ አራቱም ወንጌላት ከተነበቡ በኋላ ውኃው ተባርኮ ለተሰበሰበው ሕዝብ ይረጫል።

ጥምቀት ረቡዕ ቢውል ገሀድ ማክሰኞ፤ አርብ ቢውል ገሀድ ሐሙስ ለውጥ ሁኖ ይጦማል። ጥምቀት የሚውልባቸው አርብና ረቡዕ ስለ በዓሉ ታላቅነት ፍስክ ይሆናሉ። ጥምቀት በፍስክ ቀናት ቢውልም በዋዜማው ይጾማል።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትን ራሱ ከፈጸመ በኋላ በአብ፣ በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁ በማለት ጥምቀተ ክርስትናን እንደመሠረተ፣ ሰው ዳግመኛ ከውኃና፣ ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ እንደማይችል ያመልክተናል።

በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት መሠረት ሁለተኛ መወለድ ማለት እንደገና ወደ እናት ማሕፀን ተመልሶ በሥጋዊና በደማዊ ፈቃድ መወለድ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ረቂቅ ልደት /የነፍስን ልደት/ መወለድ ማለት ነው፡፡ ይህም ከእግዚአብሔር የመወለድ ጸጋ የሚገኘው በጥምቀትመሆኑን ያሳየናል። ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን መሠረት አድርጋ ከማይጠፋ ዘር የምንወለደውን ልደት ወንድ ልጅ በተወለደ በ፵ ቀኑ ሴት ልጅ በተወለደች በ፹ ቀኗ ታጠምቃለች፡፡እንዲሁም ዘግይው የመጡትን ግን እንደ አመጣጣቸው አንድነቱን ሦስትነቱን፣ አምላክ ሰው፤ ሰው አምላክ መሆኑ ተምረው ካመኑ በኋላ ታጠምቃቸዋለች። (ማር. ፲፮፥፲፮)፡፡

ይህ ከእግዚአብሔርየመወለድ ጸጋ የተገኘውም በሃይማኖት ነው። ክርስቶስን አምላክ ወልደ አምላክ ነው ብሎ በሃይማኖት ያልተቀበለ ከእግዚአብሔር መወለድ አይችልም። ለአመነና በሃይማኖት ለተቀበለ ብቻ የሚሰጥ ነው። ወንጌላዊው ዮሐንስ ይህንን ታላቅ የመዳን ምሥጢር እና ከእግዚአብሔር ልጅነትን የማግኘት ሥልጣን ሲያስረዳ “በስሙ ያመኑ የእግዚአብሔር ልጆች ይባሉ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው” (ዮሐ. ፩፥፲፩–፲፫) በማለት አምልቶና አስፍቶ ጽፎልናል።

ስለዚህ ጥምቀት ምሥጢር የተባለበት ምክንያት፡– 

  • ላመኑ እንጂ ላላመኑ አይሰጥምና በዐይን የሚታየው በእጅ የሚዳሰሰው ግዙፍ ነገር በመንፈስ ቅዱስ ሲለወጥ አይታይምና፣
  • ምእመናንም በጥምቀት በሚታየው የማይታየውን ጸጋ ሲቀበሉ አይታይም፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕግ ጠባዕያዊያን በመፈጽም፣ ለእናቱ እየታዘዘ አድጎ ፴ ዓመት ሲሆነው  በዘመነ ሉቃስ ጥር ፲፩ ቀን  ማክሰኞ ከሌሊቱ ዐሥር ሰዓት በባሕረ ዮርዳኖስ በዮሐንስ እጅ ተጠምቋል፡፡ “ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል”  በማለት ሰው ሁሉ ይድን ዘንድ ተጠምቆ ተጠመቁ ሲለን አርአያ ይሆነን ዘንድ ተጠመቀ፡፡ (ማር ፲፮፥፲፮)፡፡

ጌታችን የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሲሱስ ክርስቶስ ወደ ባሕረ ዮርዳኖስ ወርዶ እንደሚጠመቅ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በትንቢት መነጽርነት ዐይቶ በመዝሙሩ እንዲህ ሲል ተናግሯል “ባሕርኒ ርእየት ወጎየት ወዮርዳኖስኒ ገብአ ድኅሬሁ ወአድባር  አንፈርዐጹ ከመ ሐረጊት ወአውግርኒ  ከመ መሓስአ አባግዕ ምንተ ኮንኪ ባሕር ዘጎየይኪ ወአንተኒ ዮርዳኖስ ዘገባእከ፤ ባሕር አየች ሸሸች ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ ተራሮች እንደ ኮርማዎች ኮረብታዎችም እንደ ጠቦቶች ዘለሉ፡፡ አንቺ ባሕር የሸሸሽ አንቺ፣ ዮርዳኖስ ወደ ኋላ የተመለስሽ ምን ሆናችኋል? እናንተ ኮረብቶችስ እንደ ጠቦቶች ለምን ዘለላችሁ”  (መዝ. ፻፲፫፥፫-፮)፡፡

ጌታችን ወደ ዮሐንስ ሄዶ የተጠመቀበት ምክንያት፡-

፩. ትሕትናን ሲያስተምር ነው፡- ምነው ጌታ ፈጣሪ፤ እግዚእ ሲሆን ወደ ዮሐንስ ሄደ ቢሉ ሥጋ መልበሱ ለትሕትና ነውና፡፡ ይህ ባይሆን ዛሬ ነገሥታት ቀሳውስትን ከቤታችን መጥታችሁ አጥምቁን አቁርቡን ይሉ ነበርና፡፡

፪. ትንቢቱና ምሳሌውን ለመፈጸም (ሕዝ. ፴፮፥፳፤ መዝ.፻፲፫፥፫-፮)

ጌታችን መድኃኒታችን መጠመቅ ለምን  አስፈለገው?

፩. ጥምቀት ለሚያስፈልገን ለእኛ አርአያ ለመሆን ነው፡- እርሱ ተጠምቆ ተጠመቁ ባይለን ኑሮ ጥምቀት አያስፈልግም፡፡ አስፈላጊ ቢሆንማ ጌታ ራሱ ተጠምቆ አብነት በሆነን ነበር እንዳይሉ መናፍቃን ምክንያት አሳጣቸው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዩሐንስም ”ወአርኃወ ለነ አንቀጸ ጥምቀት ከመ ንጠመቅ፤ እንጠመቅ ዘንድ የጥምቀትን በር ከፈተልን” ሲል የጥምቀትን ምስጢር ያስረዳናል፡፡

፪. ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ፡- “አቤቱ ውኃዎች አዩህ ውኃዎች አይተውህ ፈሩ ጥልቆችም ተነዋወጡ  ወኃዎችም ጮሁ  ደመኖችም ድምጽን ሰጡ  ፍላጾችም ወጡ” (መዝ.፸፯፥፲፮-፲፯) የሚል ትንቢት ነበርና ይህ እንዲፈጸም፡፡

፫. በዮርዳኖስ ውስጥ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤ ለመደምሰስ( ሰኞ ውዳሴ ማርያም)

፬. አንድነትና ሦስትነቱን ለማስረዳት፡- ከዚህ በፊት የሥላሴ ሦስትነት በግልጽ አይታወቅም ነበር፡፡ ጌታ በዮርዳኖስ በሚጠመቅበት ጊዜ ግን ምሥጢረ ሥላሴ ግልጽ ሁኖ አብ በደመና ሁኖ የምወደው ልጄ ይህ ነው በማለቱ አብ የወልድ አባት መሆኑ ታወቀ፡፡ መንፈስ ቅዱስም የባሕርይ ሕይወቱ መሆኑ በርግብ አምሳል በራሱ ላይ ተቀምጦ ሲታይ ወልድ በተለየ አካሉ በዮርዳኖስ ሲጠመቅ ታየ ተገለጠ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በዓለ ግዝረት

ግዝረት ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ንዑሳን በዓላት አንዱ ነው፡፡ እነዚህ ንዑሳን በዓላት የሚባሉትም ስብከት፣ ብርሃን፣ ኖላዊ፣ ግዝረት፣ ቃና ዘገሊላ፣ ልደተ ስምዖን፣ ደብረ ዘይት፣ የመጋቢት ፲ መስቀልና የመስከረም ፲፯ መስቀል ናቸው፡፡

ፍቅር ወልድን ከዙፋኑ ስቦት ወርዶ ሥጋ ማርያምን ተዋሕዶ፣ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ማሕፀኗን ዓለም አድርጎ ከቆየ በኋላ ታኅሣሥ ሃያ ዘጠኝ በዘመነ ማቴዎስ ተወለደ፡፡ በተወለደ በስምንተኛ ቀኑ ሥርዓተ ኦሪትን ሊፈጽም ተገረዘ፡፡ ግዝረትን በስምንተኛው ቀን መፈጸሙ፣ በተወለደ በአርባ ቀኑ ወደ ቤተ መቅደስ መሔዱ ሕገ ኦሪትን ሊያጸና፣ ሊፈጽም፣ ምሳሌውን በአማናዊው ሊተካ እንጂ ኦሪትን ሊሽር ላለመምጣቱ እማኝ ምስክር ነው፡፡

ክርስቶስ ዘር ምክንያት ሳይሆነው እንደተፀነሰ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ማኅተመ ድንግልናዋ ሳይለውጥ እንደተወለደ እንደ ነቢዩ ሕዝቅኤል “ሳይከፈት ገብቶ ሳይከፍት እንደወጣ” ስለት ምክንያት ሳይሆነው፣ በግዝረት ምክንያት ደም ሳይፈስ በተአምራት ተገረዘ፡፡

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈ በስምንተኛው ቀን እንደ ኦሪቱ ሥርዓት ግዝረት ይፈጸምለት ዘንድ ሕፃኑ ጌታችንን ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዱት፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ ሲገረዝ የሊቀ ካህን ልጅ ነው ብለው ሊገርዙት ወደ እርሱ መጡ፡፡ ጌታችን ግን ወደ ምድር የመጣው ለትሕትና ነው እንጂ ለልዕልና አይደለምና ወሰዱት አለ /ትርጓሜ ወንጌለ ሉቃስ/፡፡ ስሙም ገና በሥጋ ሳይፀነስ የእግዚአብሔር መልአክ ባወጣለት ስም “ኢየሱስ” ተብሎ ተጠራ /ሉቃ. ፪፥፳፩-፳፬/፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ጌታ ክርስቶስ በሥጋው ግዝረትን ተቀበለ፡፡ ለአባቶች የተሰጠውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ” በማለት እንደ ተናገረው /ሮሜ. ፲፭፥፰/፣ የክብር ባለቤት መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ ግዝረት በመግባት የኦሪትን ሕግ ፈጽሟል፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም አረጋዊው ዮሴፍን “እንደ ሕጉ ልጄን እንዲገርዘውና ስሙንም እንድንሰይመው ብልህ የኾነ ገራዥ ሰው አምጣልኝ” አለችው፡፡ ጻድቁ ዮሴፍም እንዳዘዘችው የሚገርዝ ባለሙያ ይዞ መጣ፡፡ ባለሙያውም በእናቱ በንጽሕት ድንግል ማርያም ክንድ ላይ ሕፃኑ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ባየው ጊዜ እንድገርዘው በጥንቃቄ ያዙት” አላቸው፡፡ ጌታ ኢየሱስም “ባለሙያ ገራዥ ሆይ! ደሜ ሳይፈስ ልትገርዘኝ ትችላለህን? በዕለተ ዓርብ በመስቀል ስሰቀል ካልኾነ በስተቀር ደሜ አይፈስምና፡፡ ጐኔን በጦር ሲወጉኝ ያን ጊዜ ውኀና ደም ይፈሳል፡፡ ይኸውም ለአዳምና ለሚያምኑ ልጆቹ መድኀኒት ይኾናል” አለው፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችን የተናገረውን ይህን ቃል ባለሙያው በሰማ ጊዜም አደነቀ፡፡ ዕቃውንም ሰብስቦ ተነሣና ከጌታችን እግር በታች ወድቆ ሰገደ፡፡ ያንጊዜም ምላጮቹ በእጁ ላይ እንዳሉ እንደ ውኀ ቀለጡ፡፡ ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንም “ከሴቶች ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ፡፡ የማኅፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው፡፡ ይህ ልጅሽ ስለ እርሱ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት የሕያው አምላክ ልጅ ነው” አላት፡፡

ጌታችንም ባለሙያውን “እኔ ነኝ! ትገዝረኛለህን ወይስ ተውክ? ወይስ የአባቶቼ አባቶች እንዳደረጉ ላድርግ?” አለው፡፡ ባለሙያውም መልሶ”የአባቶችህ አባቶች እነማን ናቸው?”ሲል ጠየቀው፡፡ ጌታችንም አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ የሕዝቡ ሁሉ አባት እንደ ሆኑ ካስገነዘበው በኋላ “ለእነርሱም ይህ ግዝረት አስቀድሞ ከአባቴ ዘንድ ተሰጣቸው” በማለት የግዝረትን ሕግ አስረዳው፡፡ ባለሙያውም ይህን ምሥጢር ሲሰማ እኔ ከአንተ ጋር እነጋገር ዘንድ አልችልም፡፡ በአንተ ህልውና መንፈስ ቅዱስ አለና” ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት መሰከረ፡፡

በዚህ ጊዜ ጌታችን ዐይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ “አባት ሆይ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅ፣ ለያዕቆብ አስቀድሞ ግዝረትን የሰጠሃቸው፤ ያቺን ግዝረት ዛሬ ለእኔ ስጠኝ” አለ፡፡ ያንጊዜም ያለ ሰው እጅ በጌታችን ላይ ግዝረት ተገለጠ (የግዝረት ምልክት ታየ)፡፡ ከዚህ ላይ ጌታችን ወደ አባቱ ወደ እግዚአብሔር አብ ልመና ማድረሱ የለበሰው ሥጋ የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብ መሆኑንና ጸሎት ማቅረብ የሚስማማው ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ ነው እንጂ በእርሱና በአብ መካከል ልዩነት ኖሮ አይደለም፡፡

ጌታችን ድንግልናዋን ሳያጠፋ ከድንግል ማኅፀን እንደ መውጣቱ ግዝረቱም አይመረመርም፡፡ በተዘጋ ቤት ወደ ሐዋርያት እንደ ገባና እንደ ወጣ ሁሉ እርሱ በሚያውቀው ረቂቅ ጥበብ ከሥጋው ምንም ምን ሳይቈረጥ፣ ምንም ደም ሳይፈሰው መገረዙ ተገለጠ፡፡

ገራዡም የጌታችንን ቃል ከመስማቱ ባሻገር በሥጋው ላይ የተደረገውን ተአምር ባየ ጊዜ እጅግ አደነቀ፡፡ ከክብር ባለቤት ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር በታች ወድቆም ሦስት ጊዜ ሰገደና “በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ፣ የእስራኤልም ንጉሥ ነህ!” በማለት በክርስቶስ አምላክነት አመነ፡፡ ከዚህ በኋላ ያየውንና የሰማውን ሁሉ እየመሰከረ ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡- ቅዱስ ወንጌል

        ስንክሳር ጥር ፮

“ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናቸሁ” (ገላ. ፫፥፳፯-፳፰)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከእውነተኛ መምህራቸው እና አምላካቸው ክርስቶስ ይልቅ የእርሱን ቃል ባስተማሯቸው ሰዎች ማንነት መመካት እርስ በእርስ ሲከፋፈሉ ለነበሩት ለገላትያ ምእመናን “በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤ ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና፡፡ አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፣ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፣ ወንድም ሴትም የለም፣ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናቸሁ” ብሎ ነግሯቸዋል፡፡

ከዚህ መልእክት የምንረዳው እውነት አንድነታችን መሠረቱ በጥምቀት አማካይነት በእምነት በኩል የክርስቶስ አካል መሆናችን ነው፡፡ ይህም ሲባል ክርስቲያኖች ሁሉ አንድ ያደረጋቸው በክርስቶስ ማመናቸውንና በእምነት አንድ መሆናቸው እንጂ እንደማንኛውም ሰው በመልክ፣ በባሕል፣ ተወልደው ባደጉበት ቦታ እና በትምህርት ደረጃቸው አንድ ሊሆኑ እንደማይችሉ ይታወቃል፡፡ ይልቁንም ኦርቶዶክሳውያን የሆንን ሁላችን እንደማንኛውም ሰው አስቀድመው በተጠቀሱት በእነዚህ ነገሮች ሁሉ ልንለያይ ብንችልም እንኳን አንድ አምላክ ብለን ስለምናምን ከአንዲት ማኅጸነ ዮርዳኖስ እና ከአንዱ አብራከ መንፈስ ቅዱስ በአንዲት ጥምቀት አማካይነት ተወልደን የአንዱ የእግዚአብሔር ልጆች ስለሆንን፣ የክርስትና ሃይማኖትን በአንድነት ስለምንቀበል፣ በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለምኖር አንድ ነን፡፡

በአንዲት ጥምቀት አንዱ ክርስቶስን የለበሱ ክርስቲያኖቸ በሚለብሷቸው ባሕላዊ አልባሳት ምክንያት ሊለያዩ አይችሉም፤ ምድራዊው መገለጫ ከሰማያዊው ሊበልጥባቸው አይችልምና፡፡ በአንድ የፍቅር ገመድ የተሳሰሩ ምእመናን በቋንቋቸው መለያየት ምክንያት አንድነታቸው ሊፈተን አይገባውም፤ የክርስቲያኖች ዋነኛው መግባቢያ ፍቅር እንጂ ቋንቋ አይደለምና፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ ምእመናን አማካይነት “አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም” ብሎ ሲመክረን የትውልድ ዜግነታችንን ለማስካድ አይደለም፤ ከተወለድንበት ቦታ ይልቅ ክርስቲያን ሆነን የክርስትና ምግባራት ሁሉ ፈጽመን ከምንወርሳት ሰማያዊት ሀገር በእጅጉ እንደሚያንስ ለማጠይቅ እንጂ፡፡ በተመሳሳይ መልኩ “ባሪያ ወይም ጨዋ የለም” ሲልም በወቅቱ ሰዎች እርስ በእርሳቸው የተከፋፈሉባቸውን ኩነቶች ከመግለጡም ባሻገር “በክርስትና ሰው ሁሉ ሰው በመሆኑ ብቻ እኩል ነው እንጂ መበላለጥ አለመኖሩን” ለማስረዳት ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በክርስትና የሚገኘው አንድነት “ወንድ” ወይም “ሴት” የሚባል የጾታ ልዩነትን እንኳን የሚያስረሳ ፍጹም አንድ አካል መሆንን እንደሚያረጋግጥ ሐዋርያው አስረግጦ የተናገረው ተፈጥሮን ለመካድ አይደለም፡፡ በክርስቶስ አንድ የሆነ ክርስቲያን እንኳንስ በሰው ሰራሽ ነገሮች መለያየት ቀርቶ የተፈጥሮ ድንበር እንኳን ረቂቁን መንፈሳዊ አንድነት ሊያፈርሰው እንደማይቻለው ለማሳየት እንጂ፡፡

በዚሁ መሠረት አንድ መንጋ የሆነው መንፈሳዊ ቤተሰብ ደግሞ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆኖ በፍጹም የአንድነት መንፈስ ጸንቶ ይኖራል እንጂ ዘመን በተቀየረ፣ ወሬ በተወራ ቁጥር በሆነው ባልሆነው ሁሉ አንድ አይደለም፡፡ ሐዋርያው በክርስቲያኖች መካከል አንድነት እንጂ መለያየት ፈጽሞ መኖር እንደሌለበት በተማጽኖ ቃል “ነገር ግን ወንድሞች ሆይ ሁላችሁ አንድ ንግግር እንድትናገሩ በአንድ ልብና በአንድ ሐሳብም የተባበራችሁ እንድትሆኑ እንጂ መለያየት በመካከላችሁ እንዳይሆን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እለምናችኋላሁ” ሲል የሚናገረውም ለዚሁ ነው፡፡ (፩ቆሮ. ፩፥፲)፡፡

ከምንም በላይ ደግሞ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ለክርስቲያኖች የሚሰጠው በአንድነት ሕይወት ውስጥ መሆኑ በሐዋርያት ኑሮ ተረጋግጧል፡፡ በጽርሐ ጽዮን “… ሁሉም በአንድ ልብ ሆነው አብረው ሳሉ …” መንፈስ ቅዱስ እንደወረደላቸውም ቅዱስ መጽሐፋችን ይመሰክራልና(ሐዋ. ፪፥፩)፡፡ ደግሞም “በሰላም ተሳስራችሁ ከመንፈስ ቅዱስ የሚገኘውን ለመጠበቅ ትጉ፡፡ በተጠራችሁ ጊዜ ለአንድ ተስፋ እንደተጠራችሁ ሁሉ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ፡፡ እንዲሁም አንድ ጌታ አንድ እምነት እና አንድ ጥምቀት አለ፡፡ ደግሞም ከሁሉ በላይ የሆነ በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር የሁሉም አባት የሆነ አንድ አምላክ አለ” ተብለን እንደተመከርን ለአፍታም ቢሆን መዘንጋት የለብንም፡፡ (ኤፌ.፬፥፫-፯)፡፡

በጋራ በምንጸልየው ጸሎተ ሃይማኖታችንም ውስጥ “ሐዋርያት በሠሯት በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን” እንላለን፡ የቤተ ክርስቲያን ልዩ መገለጫዋ አንድነቷ ነውና፡፡ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በዋናነት በምድር ያሉት ምእመናንና ተጋድሏቸውን የፈጸሙ ቅዱሳን ኅብረት ወይም አንድነት ናት፡፡ “እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አእጹቂሃ …፤ ሥሮቿ በምድር፣ ቅርንጫፎቿም በሰማይ ያሉ” የሚለው የቅዱስ ያሬድ ትምህርትም ለዚህ ትልቅ አስረጂ ነው፡፡

ከምንም በላይ ደግሞ አማናዊውን የክርስቶስን ሥጋና ደም የተቀበሉ ሁሉ የአንዱ ክርስቶስ አካል ብልቶች ሆነዋልና አንድ ናቸው፡፡ “… ይዌልጦሙ በቅጽበት አባላተ ክርስቶስ ይኩኑ፤ በኃይለ ጥበቡ መንክር ወዕጹብ ኪኑ፤ ድንቅና ዕፁብ በሆነ በጥበቡ ኃይል የክርስቶስ አካላት ይሆኑ ዘንድ በቅጽበት ይለውጣቸዋል” እንዲል መልክአ ቁርባን፡፡ በዚህ መልኩ አንድ የሆኑ ክርስቲያኖች የአንዱ ወይኑ ግንድ (የክርስቶስ) ልዩ ልዩ ቅርንጫፎች ናቸው እንጂ የተለያዩ ተክሎች አይደሉም፡፡ (ዮሐ. ፲፭፥፭)፡፡ እናም በክርስቶስ ክርስቲያኖች የተሰኙ ሁሉ በአንድ አማናዊ እረኛ የሚመሩ አንድ መንጋ ናቸው እንጂ የሚለያዩ አይደሉም(ዮሐ.፲፥፲፮)፡፡

እንዲህ ዓይነቱ የአንድነት መንፈስ ደግሞ የሚገኘው በሥጋዊና በደማዊ ዕውቀት አይደለም፤ ይልቁንም በእምነት እንጂ፡፡ ለዚሁም ነው “ሁላችን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት ሙሉ ሰውም ወደ መሆን … እስክንደርስ ድረስ …” ተብሎ የተገለጸው፡፡ (ኤፌ. ፬፥፲፪-፲፫)፡፡ ምን ጊዜም ክርስቲያን ሆኖ ከምእመናን አንድነት በመነጠል “ሙሉ” ሊሆን የሚችል እንደማይኖር በዚህ ተገልጧል፡፡

እኛ ክርስቲያኖች “አንዲት ቤተ ክርስቲያን” ብለን የምናምነው በሰማይ ካሉት መላእክትና በአጸደ ነፍስ ካሉ ደቂቀ አዳም ጋር ጭምር አንድነት ያገኘንባትን መንፈሳዊ ኅብረት ነው፡፡ በምድር ካሉና ዕለት ዕለት ከምናያቸው ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን ጋር ያለንን ኅብረት በማቋረጥ ፈጽሞ ከማናያቸው ከእግዚአብሔር እና ቅዱሳኑ ጋር ኅብረት አለን ብንል ዘበት ይሆናል፡፡ “…ያየውን ወንድሙን የማይወድ ያላየውን እግዚአብሔርን ሊወደው እንዴት ይችላል?” እንዲል (፩ዮሐ. ፬፥፳)፡፡

በምንም ሒሳብ አብረውን ከሚያገለግሉና መንግሥተ እግዚአብሔር ለመውረስ አብረውን ከሚደክሙ ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን ኅብረት መነጠል ጤነኛነት ሊሆን አይችልም፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በአንድነት ውስጥ የሚሰጥ መሆኑን አስቀድመን ተመልክተናል፤ በተቃራኒው ደግሞ መለያየትን የሚዘራውና አንድነትን በመፈታተን ደስ የሚለው ቢኖር ጠላታችን ሰይጣን ብቻ ነው፡፡ ስለዚህም አንዴ በቋንቋ፣ ሌላ ጊዜ በዘውግ፣ ከዚያም ሲያልፍም በትውልድ መንደር እየተከፋፈሉ መናቆሩ ማንን እንደሚያስደስት ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡ ከምንም በላይ ኦርቶዶክሳዊ ቤተሰብ መሆን መቼም ሊበጠስ በማይችል መንፈሳዊ የፍቅር ገመድ እርስ በእርስ ሊያስተሳስረን ይገባል፤ ከዚህ የወጣ ክርስትና የለምና፡፡

ምንጭ፡- ጉባኤ ቃና (መጋቢት ፳፻፲ ዓ.ም)

ጌታችን ኢየሱስ ተወለደ

ዲያቆን አለልኝ ጥሩዬ

ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን በዓለም ላይ ሠልጥኖ የነበረውን ጨለማ ያስወግድ ዘንድ እግዚአብሔር አምላክ ሰው ሆነ፡፡ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው አማናዊው ብርሃን ፀሐየ ጽድቅ ክርስቶስ በሥጋ ተገለጠ፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴው እንዳለው ‹‹ብርሃን ዘበአማን ዘያበርህ ለኵሉ ሰብእ ለእለ ይነብሩ ውስተ ዓለም፤ በጨለማ ውስጥ ለሚኖር ሕዝብ ታላቅ ብርሃን ወጣላቸው››  (ኢሳ. ፱፥፪)፡፡ ቀዳሚ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው በሆነ ጊዜም ቅዱሳን መላእክት በቤተ ልሔም ተገኝተዋል፡፡ ይህንም ቅዱስ ሉቃስ ‹‹ወግብተ መጽኡ ብዙኃን ሐራ ሰማይ፤ የሰማይ መላእክት በድንገት መጡ›› በማለት ገልጾታል (ሉቃ. ፪፥፲፫)፡፡ በድንገት መባሉም አመጣጣቸው ግሩም በመሆኑ ነው፤ ቅዱሳን መላእክት ቀድሞ አመጣጣቸው ጻድቃንን ለመርዳት፣ ሰማዕታትን ከስለት ለመታደግ፣ የተቸገረውን ለማጽናት ነበር፡፡

ዛሬ ግን ስለ ሰው ፍቅር ከሰማይ የወረደውን፣ በጎል (በበረት) የተጣለውን፣ በጨርቅ የተጠቀለለውን አምላክ ከሰው ልጅ ጋር በአንድነት ለማመስገን መጡ፡፡ ‹‹ዮም አሐደ መርዔተ ኮኑ መላእክት ወሰብእ ከመ ይሰብሕዎ ለክርስቶስ ንጉሥ፤ ሰውና መላእክት፣ ንጉሥ ክርስቶስን ያመሰግኑ ዘንድ ተባበሩ›› እንዲል፡፡ መላእክት በተፈጥሯቸው የማይሞቱ (ሕያዋን) ሲሆኑ ሰው ደግሞ ሟች ነው፤ ሞት ይስማማዋል፡፡ በጌታችን ልደት ግን መላእክትና የሰው ልጆች በአንድ ማኅበር፣ በአንድ ቃል ‹‹ስብሐት ለእግዚአብሔር›› እያሉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ በአዳም ኀጢአት ምክንያት ፈርሶ የነበረው የመላእክትና የሰው ልጆች ማኅበር ከተቋረጠ ከብዙ ዘመን በኋላ በኢየሱስ ክርስቶስ ልደት እንደ ገና ተጀመረ፡፡ ይህ የምስጋና ኅብረትም ምድር እንደ ልብስ ተጠቅልላ ስታልፍ ወደ ፊት በምትመጣዋ በአዲሲቷ ዓለም፣ በአዲሱ ሰማይ፣ በአዲሱ ቤተ መቅደስ ይቀጥላል፡፡ (ራእ. ፳፩፥፩-፬)

አንድነታችን እንደማያቋርጥና በሰማይም እንደሚቀጥል አረጋዊ መንፈሳዊ ሲገልጥም ‹‹እሉሂ ወእልክቱሂ በአሐዱ ኁባሬ አልቦ ማዕከሌነ ወማዕከሌሆሙ፤ በእኛ በደቂቀ አዳም እና በቅዱሳን መላእክት መካከል ልዩነት የለም›› ይላል፡፡ ይህም የሆነው በጌታችን መወለድ ምክንያት ነው፡፡ በጌታችን ልደት ምክንያት እኛም ዳግመኛ ተወለድን፡፡ የጌታችን ልደት የእኛም የክርስቲያኖች ሁሉ ልደት ነው፡፡ ከሦስቱ የቀጰዶቅያ አባቶች አንዱ፣ ታላቁ የቤተ ክርስቲያን አባት ሊቁ ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ ይህን ምሥጢር ሲገልጥ ‹‹የክርስቶስ ልደት የመላው ሰው የልደት ቀን ነው›› ሲል መስክሯል፡፡

ሊቃውንት እንዳስተማሩን እግዚአብሔር አምላክ ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበት እና ዓለምን ያዳነበት ምሥጢር ከምሥጢራት ሁሉ በላይ ነው፡፡ ይህን ምሥጢር ከማድነቅ ሌላ ሊናገሩት አይቻልም፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም በመገረም ይህን ጥበብ እንዲህ ሲል ይገልጸዋል፤ ‹‹ምን እላለሁ? ምንስ እናገራለሁ? ከዘመን አስቀድሞ የነበረው እርሱ ሕፃን ሆኗልና፡፡ እኔ ፈጽሜ አደንቃለሁ፡፡ ከሰማየ ሰማያት በላይ የሚሆን፣ በዘለዓለማዊ ዙፋን የሚኖር እርሱ በበረት ተጣለ፡፡ ከሥጋዌ አስቀድሞ አይዳሰስ የነበረ አንዱ እርሱ በምድራውያን እጅ ተዳሰሰ፡፡ ኀጢአትን የሚያስተሰርይ እርሱን በጨርቅ ጠቀለሉት፡፡ ይህን ወዷልና፤›› (ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈ ወርቅ፣ ፷፮፥፲፯)፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስም በቅዳሴው የእግዚአብሔርን ሰው የመሆን ምሥጢር እንዲህ በማለት ገልጾታል፤ ‹‹በጐለ እንስሳ ተወድየ አሞኀ ንግሡ ተወፈየ ወከመ ሕፃናት በከየ እንዘ ይስእል እምአጥባተ እሙ ሲሳየ፤ በእንስሳት በረት ተጨመረ፤ የንጉሡንም እጅ መንሻ ተቀበለ፤ ከእናቱ ጡቶች ምግብን እየለመነ እንደ ሕፃናት አለቀሰ፤›› (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ቍ. ፲፯)፡፡

በዚህ ታላቅ በዓላችን የምናደንቀው ሌላው ምሥጢር እግዚአብሔር ወልድ በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን፣ በኅቱም ድንግልና ተፀንሶ በኅቱም ድንግልና የመወለዱ ረቂቅ ምሥጢር ነው፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይህን ድንቅ የሥጋዌ ምሥጢር ግሩም፣ ዕፁብ እያሉ ያደንቁታል፡፡ ሐዋርያውያን አበውን ተከትለው ከተነሡ የቤተ ክርስቲያን ጠባቆች መካከል አንዱ ቅዱስ ሄሬኔዎስም ፩ የእመቤታችን ዘለዓለማዊ ድንግልና፣ ፪ ድንግል ማርያም አማኑኤል ጌታን መውለዷ እና ፫ የማይሞተው አምላክ መሞት በእግዚአብሔር የዝምታ ሸማ የተጠቀለሉ ሦስት ምሥጢሮች መሆናቸውን ይናገራል፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ የተባለው አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በመጸሐፈ አርጋኖን ድርሰቱ ይህን ድንቅ የተዋሕዶ ምሥጢር በሚከተለው መልኩ ይገልጠዋል፤

‹‹ሦስቱን ደጆች ያልከፈተ የአብን ልጅ ጥበብ አደንቃለሁ፤ ያለ መለወጥ በኅቱም ድንግልና በመወለዱ፣ የመቃብሩን ደጅ ሳይከፍት በመነሣቱ፣ ደቀ መዝሙርቱ ተሰብስበው ወዳሉበት ቤት በተዘጋ ቤት በመግባቱ እና በሩን ሳይከፍት በመውጣቱ ስለነዚህም ሦስት ደጆች ልቤ አደነቀች፡፡ ከሁለቱ ይልቅ የመጀመሪያው እጅግ ያስደንቀኛል፡፡ ምክንያቱም ሁለቱን ከዚህ በፊት በመጽሐፍ ቅዱስ አውቃቸዋለሁ፡፡ የመቃብሩን ደጅ የሚመስለው ነገር አለ (ዮሐ. ፳፥፲፱)፡፡ ብልጣሶር የተባለ ዳንኤልን በአንበሶች ጕድጓድ ውስጥ በጣሉት ጊዜ ጕድጓዱን በታላቅ መዝጊያ ዘጉት፡፡ ዳንኤልም በረሃብ እንደ ተጨነቀ ልዑል እግዚአብሔር ባየ ጊዜ መልአኩን ወደ ነቢዩ ዕንባቆም ላከ (ዳን. ፮፥፲፮፲፯)፡፡ በራሱም ፀጕር አንሥቶ ተሸክሞ ወስዶ ዳንኤል ወዳለበት ጕድጓድ አገባው፡፡ ዳንኤልና ዕንባቆም እንጀራውንና ንፍሮውን በልተው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ዕንባቆምም ደጅ ተዘግቶ ሳለ ወጣ፡፡ ስለ ቤቱ ደጅም የሚመስል ነገር አለ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዶ ጴጥሮስን ከግዞት ቤት እንዳወጣው በሐዋርያት ሥራ ተጽፏል፡፡ ጴጥሮስንም ካወጣው በኋላ ደጁ ተቈልፎ ዘበኞች በሁሉ ወገን ይጠብቁ ነበር፡፡ (ሐዋ. ፲፪፥፮ለእነዚህ ለሁለቱ ደጆች ለቅዱሳን የተገኘውን ምክንያት አገኘሁ፡፡ ስለ ድንግልናሽ ደጅ እጠናለሁ፤ ግን ምክንያት አላገኘሁም፡፡ በድንግልና የኖረች ሴትም አላየሁም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ነገር ሆኖ አያውቅም፡፡ ኢኮነ እምቅድመ ወኢኮነ እምድኅረ ከዚህ በፊት አልተደረገም፤ ከዚህ በኋላም አይደረግም›› (አርጋኖን ዘቀዳሚት)፡፡

በዓለ ልደት፣ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል እርቅ የተፈጸመበት በዓላችን ነው፡፡ ለሞት ከመገዛት የዳንበት፤ ጨለማው ተወግዶልን የብርሃን ልጆች የሆንበት፤ የእባብ ራስ የተቀጠቀጠበት፤ ከምድር ወደ ሰማይ ያረግንበትና ከመላእክት ጋር ሆነን ለእግዚአብሔር ምስጋና ያቀረብንበት፤ ከነቢያት ኅብረት ጋር አንድ የሆንበት በዓል ነው፡፡ ድንቅ የተዋሕዶ ምሥጢር የተፈጸመበትን ይህን ልዩ በዓል በመንፈሳዊ ሥርዓት ማክበር ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር

ራስን መግዛት

በመ/ር በትረ ማርያም አበባው(የመጻሕፍተ ብሉያትና የመጻሕፈተ መነኮሳት መምህር)

ራስን መግዛት ማለት ራስን ከክፉ ነገር መጠበቅ፣ ሰውነትን መቆጣጠር፣ ራስን ከኃጢኣት ማራቅ ማለት ነው። ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች በላከው መልእክቱ ራስን መግዛት የመንፈስ ፍሬ እንደሆነ ገልጧል። (ገላ. ፭፥፳፪)

ቅዱስ ጴጥሮስም በ(፪ኛ ጴጥ.፩፣፮) “በበጎነትም ዕውቀትን በዕውቀትም ራስን መግዛትን ራስንም በመግዛት መጽናትን በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰል እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማችነትን መዋደድ በወንድማማችም መዋደድ ፍቅርን ጨምሩ” ብሎ ስለ ራስን መግዛት ተናግሯል።

ራስን መግዛት  ለምን? ብለን ስንጠይቅ በዋናነት ራስን ከኃጢኣት ለመጠበቅ ነው። ኃጢኣት በሦስት መንገድ ይሠራል። ይኸውም በኀልዮ (በማሰብ)፣ በነቢብ (በመናገር) እና በገቢር (በድርጊት) ነው። ኀልዮ በመጽሐፈ መነኮሳት ትርጓሜ ላይ እንደተጻፈው ሁለት ደረጃዎች አሉት። እኒህም ነቅዐ ኀልዮ እና ቁርጽ ኀልዮ ናቸው።

ነቅዐ ኀልዮ ማለት የሰው ልጅ በአምስቱ የስሜት ሕዋሳቶቹ ማለትም (መዳሰስ፣ ማሽተት፣ ማየት፣ መስማት፣ መቅመስ) አማካኝነት ለመጀመሪያ ጊዜ የሚታሰበው ቅጽበታዊ ሐሳብ ነው። ይህን በስሜት ሕዋሳታችን አማካኝነት ያሰብነውን ቅጽበታዊ ሐሳብ ደጋግመን በሕሊናችን ስናመላልሰው ደግሞ ቁርጥ ኀልዮ ይባላል። በሕሊናችን የታሰበውን ሐሳብ ስንናገረው ደግሞ ነቢብ ይባላል። ያሰብነውን ሐሳብ እና የተናገርነውን ነገር ወደ ተግባር ስናውለው ደግሞ ገቢር ይባላል። ስለዚህ በሦስቱም መንገድ ኃጢኣት ወደ ሰውነታችን እንዳይገባ ራሳችንን መግዛት አለብን ማለት ነው።

በኀልዮ (በማሰብ) የሚመጣ ኃጢኣት እንዳይጥለን ከፈለግን የስሜት ሕዋሳቶቻችንን መቆጣጠር ነው። ይህም ማኅሌታዊው ቅዱስ ያሬድ “ዐይን ይጹም ዕዝንኒ ይጹም፣ እምሰሚዐ ኅሡም፤ ዓይን ክፉ ነገር ከማየት፣ ጆሮም ክፉ ነገር ከመስማት ይከልከል” ያለው ነው። የሰው ልጅ ዓይኑን ክፉ ነገር እንዳያይ ከተቆጣጠረው፣ ጆሮውንም ክፉ ነገር እንዳይሰማ፣ እጁን ክፉ ነገር እንዳይዳስስ፣ አፉን ክፉ እንዳይናገር፣ አፍንጫውን ክፉ እንዳያሸት ከተቆጣጠረው በኀልዮ የሚመጡ ኃጢአቶችን መቀነስ ይችላል።

ክፉ የሚባለው የእግዚአብሔርን ሕግ የሚያስሽር ሁሉ ነው። አንድ ሰው ዝሙትን የሚያሳስብ ንግግር በጆሮው ከሰማ ወይም ዝሙትን የሚያሳስብ ነገር በዓይኑ ካየ ከዚያ ቀጥሎ “ነቅዐ ሀልዮ” ይከተለዋል። ይህም ወደ ቁርጥ ሀልዮ ያድጋል። (ማቴ. ፭፣፳፷)

“እኔ ግን እላችኋለሁ ሴትን ዐይቶ የተመኛት ሁሉ ፈጽሞ በልቡ አመነዘረባት” ይላል። ማመንዘር ደግሞ ከ፲ሩ ሕግጋት አንዱ የሆነውን (ዘጸ. ፳፥፳፬) “አታመንዝር” የሚለውን ሕግ አስሽሮ ወደ ሲኦል የሚመራ ነው። ስለዚህ የሰው ልጅ ፍጻሜያቸው የእግዚአብሔርን ሕግ የሚያስሽሩ ነገሮችን ከማየት፣ ከመስማት፣ ከመዳሰስ፣ ከማሽተት እና ከመቅመስ ራሱን መከልከል አለበት ማለት ነው።

በተጨማሪ ነገራተ እግዚአብሔርን በማሰብ፣ ነገረ ስቅለቱን ሁል ጊዜ በማሰብ፣ ጣዕመ መንግሥተ ሰማያትን እና ምረረ ገሐነመ እሳትን አዘውትሮ በማሰብ ከክፉ ሐሳብ እንላቀቃለን። በእርግጥ አንዳንድ ሐሳቦች ለብዙ ዘመናት ይፈትኑን ይሆናል። ነገር ግን እኛም እነዚያን ለማራቅ ተስፋ ሳንቆርጥ እስከ መጨረሻው መታገል ይገባል። የስሜት ሕዋሳቶቻችንን ከክፉ ነገር መጠበቅ ብቻ ሳይሆን በምትኩ መንፈሳዊ ነገርን ልናይባቸው፣ ልንሰማባቸው፣ ልንዳስስባቸው፣ ልንናገርባቸው ይገባል።

ዐይን ቅዱሳት ሥዕላትን፣ መንፈሳዊ መጻሕፍትን ይመልከት። “…የእግዚአብሔርን መድኃኒት እዩ” እንዲል (፪ኛዜና. ፳፣፲፯)፡፡ “ኑ የእግዚአብሔርን ሥራ እዩ” (መዝ. ፷፮፣፭)፡፡ ጆሮ የእግዚአብሔርን ቃል ይስማ። “ቃሌን ስሙ” (ዘኊ. ፲፪፣፮) እንዲል። አፋችን እውነትን ይናገር።  “የእግዚአብሔርን ምሥጋናና ኃይሉን ያደረገውንም ተአምራት ተናገሩ” (መዝ. ፸፰፣፬) እንዲል።

በነቢብ (በመናገር) ከሚሠሩ ኃጢአቶች መከልከል የምንችለው ባለመናገር ነው። “ከቃልህ የተነሣ ትጸድቃለህና ከቃልህም የተነሣ ትኮነናለህና” (ማቴ. ፲፪፣፴፯) እንዲል። መጽሐፈ መነኮሳት ላይ ያለ አንድ ታሪክ አለ። ይኸውም በአንድ ወቅት ሙሴ ጸሊምን ሰዎች መጥተው ክፉ ክፉ ቃል ተናገሩት። እርሱም ምንም ሳይመልስ ዝም አለ። በኋላ ደቀ መዛሙርቱ አባታችን ያንን ሁሉ ክፉ ክፉ ቃል ስትሰደብ ምንም አልተሰማህም ወይ? ብለው ይጠይቁታል። እርሱም ሲመልስ “በእርግጥ ስሰደብ መልሰህ ስደባቸው መልሰህ ስደባቸው የሚል ስሜት መጥቶብኝ ነበር፤ ነገር ግን እንዳልናገር አፌን ተቆጣጠርኩት” ብሏቸዋል፡፡ (መጻሕፍተ መነኮሳት)፡፡

ንጽሐ ሥጋ የሚጀመረው በአርምሞ ነው። አርምሞ ማለትም ክፉን ቃል አለመናገር ማለት ነው። አንድን ነገር ከመናገራችን በፊት ነገሩን በቃለ እግዚአብሔር ሚዛንነት ለክተን እንናገር። አለበለዚያ ግን ዝም እንበል። “አቤቱ ለአፌ ጠባቂ፣ ለከንፈሮቼም ጽኑዕ መዝጊያን አኑር” (መዝ.፻፵/፻፵፩፣፫) እንዲል። ሌላውን ሰው የማያሳዝን ቃል ልንናገር ይገባል። እኛም ተናግረን የምንጠቀምበት ሰሚውም ሰምቶ የሚጠቀምበትን ነገር ልንናገር ይገባናል። እንዲህ ስናደርግ ራሳችንን ገዛን ይባላል።

በገቢር (በድርጊት) ከሚመጡ በደሎች ለመራቅ ደግሞ አንዳንድ ጊዜ በመሸሽ ሊሆን ይችላል። ለምሳሌ ዮሴፍ በጲጥፋራ ሚስት የተፈተነውን ፈተና ያመለጠው በመሸሽ ነው። (ዘፍ. ፴፱፣፯) “ከዚህ በኋላ የጲጥፋራ ሚስት በዮሴፍ ላይ ዓይኗን ጣለች። ከእኔም ጋር ተኛ አለችው” እንዲል። አስተውሉ ዮሴፍ የተጠየቀው የገቢር ኃጢአትን እንዲሠራ ነው። ነገር ግን ዮሴፍ እግዚአብሔርን አልበድልም ብሎ ሸሽቶ አምልጧል። በዚህም ምክንያት “እግዚአብሔርም ከዮሴፍ ጋር ነበረ ምሕረትንም አበዛለት” ተብሎ ተጽፎለታል። (ዘፍ. ፴፱፣፳፩)

ስለዚህ በጠቅላላው ራስን መግዛት ማለት እኛን ከእግዚአብሔር ከሚለዩን ነገሮች መከልከል፣ ኃጢኣት ወደ ሰውነታችን እንዳይገባ መቆጣጠር ነው። ስለሆነም የሰው ልጅ ሥጋዊ ፍላጎቱ ወይም ስሜቱ የሚገዛው ሳይሆን ሥጋዊ ፍላጎቱን ወይም ስሜቱን የሚገዛ መሆን አለበት። “ኃጢአትን የሚያደርግ ሁሉ የኃጢአት ባርያ ነው”።(ዮሐ.፰፣፴፬)

 አስተውል ሰው ኃጢአተኛ ከሆነ የኃጢአት ባርያ ይሆናል እንጂ የራሱ ገዢ አይሆንም።  “በሚሞት ሥጋችሁ ኃጢአት አይንገሥ” (ሮሜ.፮፣፲፪) እንዲል። ራሳችንን ካልገዛን በራሳችን ሌላ ኃጢአት ይነግሥብናል። ሌላው ራስን መግዛት የሚባለው ከኃጢአት መራቅ ብቻ ሳይሆን መልካም ሥራንም መሥራት ነው። “እንግዲህ በጎ ለማድረግ ዐውቆ ለማይሠራው ኃጢአት ነው” (ያዕ. ፬፣፲፯)። ይህም ማለት በጎ ትምህርትን፣ በጎ ዕውቀትን ገንዘብ አድርገን ወደ ተግባር ካልለወጥነውም ኃጢአት ይሆንብናል። አንድ ንጉሥ ወይም ገዢ የሚመሰገነው ሕዝቡን ከውጭ ወራሪ ከውጭ ጠላት በመጠበቁ ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን በመልካም አስተዳደርም በማስተዳደሩ ነው። ስለዚህ ማንኛውም የሰው ልጅ ራሱን ሲገዛ ከኃጢአት መጠበቅ ብቻ ሳይሆን ጽድቅንም መሥራት ይኖርበታል።

ራስን ለመግዛት ጾም ትልቅ አስተዋጽኦ አለው። ሊቁ “ኀዲገ መብልእ ለዘተክህሎ፣ ሐራዊ በጸብእ ኢይኄይሎ ወንጉሥ በላእሌሁ ኢሀሎ፤ ምግብን መተው የቻለን ሰው ወታደር በጠብ አይችለውም። በእርሱም ላይ ንጉሥ የለም” ብሏል። ይህም ማለት ሰው ሲጾም ሲጸልይ በራሱ ላይ የተሾመ የራሱ ንጉሥ ይሆናል ማለት ነው። ሰው ራሱን ከገዛ ዓለምን መግዛት ይችላል። ስለዚህ ክፉ ከማሰብ፣ ክፉ ከማድረግ፣ እንዲሁም ክፉ ከመሥራት በመጠበቅ ራስንም በመግዛት ለእግዚአብሔር የምንመችና እንደ ቃሉም የምንመላለስ ሆነን መገኘት ከእኛ ኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡

ራስን በመግዛት ከክፉ ተጠብቀን የመንግሥቱ ወራሾች ያደርገን ዘንድ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ አሜን፡፡

 

 

ግቢ ጉባኤያት እና የጊዜ አጠቃቀም

በእንዳለ ደምስስ

እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ይጠቀሙበት ዘንድ ከሰጣቸው ሥጦታዎች ውስጥ አንዱ ጊዜ ነው፡፡፡ ሁሉንም በሥርዓት አበጅቶታልና የተሰጠውን ሥጦታ በአግባቡ የመያዝና የመጠቀም ኃላፊነት ደግሞ ከሰው ልጆች ሁሉ ይጠበቃል፡፡ “የሠራው ሥራ ሁሉ በጊዜው መልካም ነው” እንዲል (መክ.፫፥፲፩)፡፡

ጊዜ ቆሞ አይጠብቀንም፡፡ ሴኮንድ ወደ ደቂቃ፣ ደቂቃ ወደ ሰዓት፣ ሰዓታት ወደ ቀን፣ ቀን ወደ ሳምንት፣ ሳምንታት ወደ ወራት፣ ወራት ወደ ዓመት፣ …. ዘመን ዘመንን እየተካ ትውልድ ያልፋል ትውልድ ይተካል፡፡ ጊዜ ይመጣል ጊዜ ይሄዳል፡፡ በዚህ እግዚአብሔር እንኖርበት ዘንድ በሰጠን ዕድሜአችን ደግሞ ለተፈጠርንበት ዓላማ መኖር ከሰው ልጆች ይጠበቃል፡፡ ነገር ግን ምን ያህል ተጠቅመንበታል? ስንል ከተጠቀምንበት ይልቅ ጊዜአችንን በዋዛ ፈዛዛ እንዳሳለፍነው እንረዳለን፡፡

ከሥነ ፍጥረት ጀምሮ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት ጠብቀው እንደ ቃሉም ተመላልሰው በሥራ በመግለጥ ወደዚህች ምድር የመጡበትን ተልእኮ አጠናቀው ለትውልድ አርአያ ሆነው ያለፉ አበው ዛሬም ድረስ በቅዱሳት መጻሕፍቶቻችን፣ በኑሯችን ሁሉ ስንጠቅሳቸው እንኖራለን፡፡ ጊዜአቸውን በአግባቡ መልካምን በማድረግ አልፈውበታልና በቃል ኪዳናቸው ተጠቃሚዎች ነን፡፡ ሌላው ግን በቀልድና በጨዋታ፣ እንዲሁም ከጽድቅ ይልቅ ለኃጢአት በመትጋት ዘመኑን ይጨርሳል፡፡ ሁለቱም በበጎነትና በመጥፎነት ለእኛ እንደ ምሳሌ ሆነው የምናነሳቸው ናቸው፡፡ “እናንተም ልትድኑበት የተማራችሁትን የእውነት ቃል ሰምታችሁና አምናችሁ ተስፋ ባደረገላችሁ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፡፡” (ኤፌ. ፩፥፲፫) እንዲል በፍቅር እግዚአብሔርን በማገልገል ጊዜያቸውን ለመልካም ነገር ተጠቅመው ለተጠሩበት ታምነው ለሌሎች ምሳሌ ሆነው አልፈዋል፡፡

በተቃራኒው ደግሞ “ለኃጠአት ትገዙ በነበረበት ጊዜ ከጽድቅ ነጻ ነበራችሁና፤ በዚያን ጊዜ ሥራችሁም እነሆ ዛሬ ታፍሩበታላችሁ፤ መጨረሻው ሞት ነውና” ይላል እግዚአብሔር በሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ላይ አድሮ፡፡ (ሮሜ. ፮፥፳፩)፡፡ ስለዚህ ጊዜአችንን በአግባቡ ተጠቅመን በረከት እንድናገኝ መትጋት ከኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡

ወደ መነሻ ሐሳባችን ስንመለስ ጊዜን በአግባቡ መጠቀም ከሁሉም የሚጠበቅ ቢሆንም በተለይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚገኙ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ላይ ትኩረታችንን እናደርጋለን፡፡

ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገቡ ወጣቶች ከሚቸገሩበት ጉዳይ አንዱ የጊዜ አጠቃቀማቸውን መቆጣጠር አለመቻላቸው ነው፡፡ ከቤተሰብ መራቃቸው ነጻነት ስለሚሰጣቸው ለተለያዩ ችግሮች በመጋለጥ ውጤታማ ሳይሆኑ ይቀራሉ፡፡ ከትምህርታቸውም ሆነ ከመንፈሳዊ ሕይወታቸው ሳይሆኑ ባክነው ይቀራሉ፡፡

“ወደ ግቢ ጉባኤያት ገብታችሁ ለምን አትማሩም?” ሲባሉም የተለያዩ ምክንያቶችን ያቀርባሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን ብንመለከት፡-

፩.የጥናት ጊዜአችንን ይሻማብናል፡-

ተማሪዎች ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከገቡ በኋላ በግቢ ጉባኤ ላይ እንዳይሳተፉ በዋነኛነት የሚጠቅሱት “ጊዜአችንን ይሻማብናል” በማለት እንደ ማምለጫ የሚጠቀሙበት አባባል ነው፡፡ ግቢ ጉባኤ ገብተው ለሥጋዊም ሆነ ለነፍሳቸው የሚሆን ስንቅ ይዘው እንዲወጡ ለሚመክሯቸው ሁሉ እንደ ኋላ ቀር በመቁጠር ሲያላግጡ ይስተዋላል፡፡ እግዚአብሔርን መፍራት በውስጣቸው ስለሌለ ዓለም ትናፍቃቸዋለች፡፡ ከትምህርት በኋላም ለጥናት ጊዜአቸውን ከመስጠት ይልቅ ሥጋዊ ፍላጎታቸው ወደሚመራቸው በመሄድ የሚሹትን ያከናውናሉ፡፡

“የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ” (መክ.፲፪፥፩) የሚለውን ቃል ይዘነጋሉ፡፡ ራሳቸውን ከእግዚአብሔር በመለየት በተሰጣቸው የንስሓ ጊዜ ሁሉን ልጨብጥ፣ ሁሉን ላድርግ በማለት በወጣትነት ዘመናቸው ኃጢአት ለመሥራት ይተጋሉ፡፡ ፍጻሜአቸውም ያማረ አይሆንም፡፡ በትምህርታቸው የሚፈለገውን ያህል ሳይሆኑ፣ ከእግዚአብሔርም ጋር ያላቸው ግንኙነት ተቋርጦ ተመርቀው ቢወጡም በተመደቡበት ሁሉ ሕዝብን ከማገልገል ይልቅ ራሳቸውን የሚወዱ፣ ለክፉ ሥራ የሚተጉ ሆነው ይገኛሉ፡፡

በአግባቡ በግቢ ጉባኤ ውስጥ የተሚሳተፉ ተማሪዎች ግን ጊዜአቸውን በአግባቡ በመጠቀማቸው፣ ለማገልገልና ለመገልገል ራሳቸውን ያዘጋጁ በመሆናቸው እግዚአብሔርን አጋዥ አድርገው በማስተዋል ስለሚጓዙ ውጤታማ ሆነው ለመውጣት አይቸገሩም፡፡

፪. የመዝናኛ ጊዜ ያስፈልገናል፡-

በትርፍ ጊዜያቸው የእግዚአብሔርን ቃል ከመስማትና ከማንበብ በመራቅ “አእምሯችንን እናድስ” በሚል ፈሊጥ ጊዜአቸውን ለጨዋታና ለማኅበራዊ ሚዲያ በመስጠት ባክነው የሚቀሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ በማኅበራዊ ሚዲያዎችም ለሥጋዊ ምኞታቸው የሚቀርባቸውን በማየትና በመስማት ኃጢአትን ይለማመዳሉ፡፡ ከተቃራኒ ጾታ አልፈው ለተመሳሳይ ጾታ እስከመጋለጥ የሚደርሱ በርካቶች ናቸው፡፡

ከትምህርት በኋላ ራሳቸውን ለማዝናናት በሚያደርጉት ጥረትና ሩጫ ውስጥ በተቋሙ ዙሪያ የሚገኙ የመዝናኛ ሥፍራዎች ማለትም ጫት ቤቶች፣ ከሲጋራ ጀምሮ ሐሺሽ፣ ጭፈራ ቤቶችና የአልኮል መጠጥ መሸጫ ቦታዎች በስፋት በመኖራቸው ጊዜአቸውን እንዲሁ በማይጠቅምና ዓላማን በሚያስረሳ አካሄድ እንዲጓዙ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ገና አንደኛ ዓመት ሳይጨርሱ ለመባረር ሲገደዱ መመልከት የተለመደ ነው፡፡ ቤተሰብ ልጄ ተምሮና ሥራ ይዞ ራሱንም ቤተሰቡንም ይረዳል ብሎ ሲጠብቅ መልሶ የቤተሰብ ሸክም ሆነው ይቀራሉ፡፡ ለዚህ ሁሉ ችግር ለመጋለጣቸው ዋነኛው ምክንያት ጊዜአቸውን መልካም ለሆነ እና ለተጠሩበት ዓላማ ባለማዋላቸው የተነሣ ነው፡፡

. የጓደኛ ተፅዕኖ፡-  

በተለያየ ምክንያት በሚኖረን አብሮ የመኖር መስተጋብር ውስጥ ጓደኛ ልናፈራ እንችላለን፡፡ ጓደኛ ያልነው ሰው ምን ዓይነት ሰው ነው? ፈሪሃ እግዚአብሔር ያደረበት፣ በመልካም ጎዳና የሚጓዝና አርአያ ሊሆነን የሚችል ሰው ነው? ብለን መፈተሽ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል፡፡ በተለይም ወጣቶች የጓደኛ ምርጫ ላይ ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ በግቢ ጉባኤያት ውስጥ የሚሳተፉ ተማሪዎችም ከማይመቹ ጓደኞች ሊርቁና ክፉውንና ደጉን በመለየት ትክክለኛውን መንገድ እግዚአብሔር እንዲያሳያቸው በጸሎት በመትጋት በአገልግሎት በመጽናትና ለዓላማቸው ታማኝ በመሆን በማስተዋል ሊጓዙ ይገባቸዋል፡፡

በጓደኛ ተፅዕኖ ምክንያት ከዓላማቸው እንዳይዘናጉ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መጠለል፣ ድምጿንም ለመስማት ራሳቸውን ማዘጋጀት፣ ለትምህርታቸውና ለአገልግሎት ቅድሚያ መስጠት ይጠበቅባቸዋል፡፡

፬. የቴክኖሎጂ ውጤቶች፡-

ዓለም ዓላማን ሊያስቱ የሚችሉ፣ ትውልድን ከማነጽ ይልቅ በቴክኖሌጂ ስም ወጣቶችን ሊያማልሉና ወደ ጥፋት ጎዳን ሊወስዱ የሚችሉ ነገሮችን በመፈብረክ ተጠምዳ ትውላለች፡፡ በዚህም ምክንያት ወጣቶች ጊዜአቸውን እንዲያባክኑ ዕድሉን ታመቻቻለች፡፡ አንድን የቴክኖሎጂ ውጤት በተገቢው ጊዜና ቦታ ለአስፈላጊ ነገር ብቻ መጠቀም መልካም ቢሆንም ይህንን በመዘንጋት ቀኑን ሙሉ ለሚረባውም፣ ለማይረባውም ነገር ተጠምዶ መዋል ለሱሰኝነት ያጋልጣል፡፡ በተለይም የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ጊዜአቸውን ከማባከንና ለሱሰኝነት ሊያጋልጧቸው ከሚችሉ የቴክኖሎጂ ውጤቶች መራቅ፣ አስፈላጊ ሲሆን ለትምህርታቸው እገዛ ሊያደርጉላቸው የሚችሉትን ብቻ በተገቢው ጊዜ መጠቀም ይገባቸዋል፡፡

ከላይ በጥቂቱ ለማንሳት የሞከርናቸው ጉዳዮች በአብዛኛው በወጣቶች ላይ በተለይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጎልተው የሚታዩ ችግሮች እንደመሆናቸው መጠን ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሹ ናቸው፡፡

በግቢ ጉባኤያት ውስጥ የሚሳተፉ ወጣቶችም ጊዜአቸውን ለትምህርታቸውና ለአገልግሎት በመስጠት በጾም፣ በጸሎትና በስግደት በመጽናት ወደ እግዚአብሔር በመጸለይ ያለቻቸውን ጊዜ በዕቅድ በመምራት ተጠቃሚ መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡

ለትምህርት፣ ለጸሎት፣ ለአገልግሎት የሚያውሉትን ጊዜ በመንደፍ በዕቅድ ራሳቸውን የሚመሩ ተማሪዎች ውጤታማ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ ለዚህም ትልቁ ምስክርና ማረጋገጫ የሚሆነን በየ ከፍተኛ ተቋማቱ በቆይታቸው ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚዎች መሆናቸውና ቁጥራቸውም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ ነው፡፡

በከፍተኛ ውጤት ለመመረቃችሁ ምክንያት ምንድነው ተብለው ሲጠየቁም በግቢ ጉባኤያት ውስጥ በመሳተፋቸው በሥነ ምግባር እንዲታነጹና ጊዜአቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ እንደረዳቸው ይናገራሉ፡፡ ጊዜአቸውን በአግባቡ ተጠቅመውበታልና ከኅሊና ወቀሳ ነጻ ናቸው፡፡ በዚህም ድርጊታቸው ከራሳቸው አልፈው ቤተ ክርስቲያንንና ወላጆቻቸውን ያስመሰግናሉ፡፡ ተመርቀውም ሲወጡ በዕውቀት የበለጸገ፣ በሥነ ምግባር የታነጸ ትውልድ ሆነው ስለሚወጡ በተሠማሩበት የሥራ መስክም ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ኃላፊነታቸውን ይወጣሉ፡፡ በዚህም ጊዜን በአግባቡ መጠቀም የሚያስገኘውን ጥቅም ሌሎች እንዲረዱት አርአያነታቸውን ያስመሰክራሉ፡፡ ከእነርሱ በኋላ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚገቡ ተማሪዎችም ምሳሌ ይሆናሉ፡፡

በአጠቃላይ ራስን በሃይማኖት አቅንቶ፣ በአገልግሎት አንጾና በጾም ጸሎት በርትቶ ጊዜን በአግባቡ መጠቀም ለውጤት እንደሚያበቃ ከግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ተሞክሮ እንረዳለን ማለት ነው፡፡ ወደፊትም ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገቡ ተማሪዎችም ይህንን በመረዳት ጊዜአቸውን በአግባቡ በመጠቀም ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ ሊጠቀሙበት ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር