“በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” (ማቴ. ፲፯፥፬)

“በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” (ማቴ. ፥፬)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት ጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ብርሃነ መለኮቱን፣ ክብረ መንግሥቱን መግለጡን በማሰብ በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በዓሉ በድምቀት ታከብራለች፡፡ ደብረ ታቦር ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት በዓላት መካከልም አንዱ ነው፡፡

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊሊጶስ ቂሳርያ አገር በደረሰ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን “የሰውን ልጅ ሰዎች ማን ይሉታል?” ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም “መጥምቁ ዮሐንስ ነው የሚሉ አሉ፤ ሌሎችም ኤልያስ፣ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ” አሉት፡፡ እርሱም “እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?” ሲል ሐዋርያትን ጠየቃቸው፡፡ ስምዖን ጴጥሮስም መልሶ “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፡- “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ ብፁዕ ነህ፤ በሰማይ ያለው አባቴ ነው እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና …” ብሎታል፡፡ (ማቴ. ፲፮፥፲፫-፲፱)

ከዚያም በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳሌም ይሄድ ዘንድ ከሽማግሌዎችና ከካህናት አለቆች ከጻፎችም ብዙ መከራ ይቀበልና ይገደል ዘንድ በሦስተኛውም ቀን እንደሚነሣ ለደቀ መዛሙርቱ ይነግራቸው ጀመረ፡፡ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ግን የሞቱን ነገር ሲሰማ “አቤቱ ይህ አይሁንብህ፡ ከቶም አይድረስብህ” እያለ ይከለክለው ጀመረ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ምስጢር ተሰውሮበታልና ጌታችንን ተከላለከለው፡፡ (ማቴ. ፲፮፥፲፫-፳፫) ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን መለስ ብሎ ጴጥሮስ “አንተ ሰይጣን ከኋላዬ ሂድ ዕንቅፋት ሆነህብኛል፤ የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታሰብምና” በማለት ገሰጸው፡፡

ከስድስት ቀን በኋላም ቅዱስ ጴጥሮስን፣ ቅዱስ ያዕቆብንና ወንድሙን ቅዱስ ዮሐንስን ይዞ ሌሎቹን ደቀ መዛሙርቱን ደግሞ በእግረ ደብር ትቶ ወደ ደብረ ታቦር ተራራ ወጣ፡፡ በዚያም መልኩ በፊታቸው ተለወጠ፤ ፊቱም እንደ ፀሐይ አበራ፤ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከሙታን፣ ሞትን ካልቀመሱት ነቢያት መካከል ደግሞ ከብሔረ ሕያዋን ነቢዩ ኤልያስ መጥተው ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው፡፡

ሦስቱም ደቀ መዛሙርት ባዩት ነገር ተደነቁ፡፡ በዚያም መኖር መልካም እንደሆነ አስተዋሉ፡፡ ከመካከላቸውም ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ “አቤቱ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ ሦስት ቤቶችን በዚህ እንሥራ፤ አንዱን ለአንተ፣ አንዱንም ለሙሴ፣ አንዱንም ለኤልያስ” አለው፡፡ እርሱ ገና ይህን ሲናገር ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፡፡ አብ በደመና ውስጥ ሆኖ “የምወደው እርሱም ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” የሚል ቃል መጣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ያዩትንና የሰሙትን መቋቋም አልቻሉም፣ እጅግም ፈርተው ነበርና በግምባራቸው ወድቀው ሰገዱ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርቦ ዳሰሳቸውና “ተነሡ አትፍሩም” አላቸው፡፡ ዐይኖቻቸውን አቅንተው ቢያዩ ከጌታችን በስተቀር ያዩት ሌላ ማንም አልነበረም፡፡ ከተራራውም ሲወርዱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “የሰው ልጅ ከሙታን ተለይቶ እስኪነሣ ደረስ ያያችሁትን ለማንም አትናገሩ” ብሎ አዘዛቸው፡፡

እነርሱ ግን ባዩትና በሰሙት ሁሉ ተመስጠዋልና ከአምላካቸውና ከነቢያቱ ጋር በዚያ አብሮ መኖርን ናፈቁ፡፡ የረቀቀው ገዝፎ፣ የራቀው ቀርቦ ምስጢር እየተገለጠላቸው ዓለምን ንቀው ይኖሩ ዘንድ ተመኙ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስ ግን ጊዜው ሲደርስ በጊዜው ሁሉን ያከናውናልና ከዚህ በላይ ምስጢሩን መሸከም አይችሉምና ይዟቸው በእግረ ደብር ወዳሉት ሐዋርያት ወሰዳቸው፡፡ ከተራራው ሲወርዱም ልዩ ልዩ ጥያቄዎችን እየጠየቁትና እየመለሰላቸው ምስጢር እየገለጠላቸው ወርደዋል፡፡  

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምስጢረ መንግሥቱን ለምን በደብረ ታቦር ተራራ ገለጠ ቢሉ፡- ትንቢቱንና ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡

፩. ትንቢቱን ለመፈጸም፡- በነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ምስጢረ መንግሥቱን ለደቀ መዛሙርቱ ገልጦላቸዋል፡፡ “ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፤ ስምህን ያመሰግናሉ” እንዲል (መዝ. ፹፰፥፲፪)፡፡

. ምሳሌውን ለመፈጸም፡- ታቦር ተራራ ባርቅ ሲሳራን ድል አድርጎበታል (መሳ. ፬፥፮)፡፡ “የእስራኤል ልጆች በእግዚአብሔር ፊት እንደገና ክፉ ሥራ ሠሩ፡፡ እግዚአብሔርም በአሶር በነገሠው በከነዓን ንጉሥ በኢያቡስ እጅ አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ የሠራዊቱም አለቃ ሲሣራ ዘጠኝ መቶ የብረት ሰረገሎች ነበሩትና እስራኤላውያንን ሃያ ዓመት ያስጨንቃቸው ነበር፡፡ (መሳ. ፬፥፩-፫)፡፡ እግዚአብሔርም እስራኤላውያን ከዚህ ቀንበር ይላቀቁ ዘንድ አመለከታቸው፡፡ (፩ቆሮ. ፲፥፲፫)፡፡ እስራኤላውያን ወደ ፈጣሪያቸው በጮኹ ጊዜም ነቢይቱን ዲቦራን ተጠቅሞ የማሸነፊያ መላውን አመለከታቸው፡፡ እግዚአብሔር በነቢይቱ በዲቦራ በኩል ለእስራኤል ንጉሥ “ሔደህ ወደ ታቦር ተራራ ውጡ” ብሎ አዞት ነበርና ንጉሡ ዐሥር ሺሕ ብረት ለበስ ያልሆነ እግረኛ ሠራዊት ይዞ ደብረ ታቦርን ተማምኖ በተራራው ላይ መሸገ፤ ጦርነቱም ሳይጀመር አለቀ፡፡ ምክንያቱም “እግዚአብሔርም ሲሣራን ሰረገሎቹንም ሁሉ ሠራዊቱንም ሁሉ ከባርቅ ፊት በሰይፍ ስለት አስደነገጣቸው፡፡ ሲሣራም ከሰረገላው ወርዶ በእግሩ ሸሸ” (መሳ. ፬፥፲፭)፡፡ እስራኤላውያንም በእግዚአብሔር አጋዥነት በታቦር ተራራ ላይ የሃያ ዓመት የግፍና የሰቀቀን አገዛዝን አስወገዱ፡፡

ለምን ሦስቱን ሐዋርያት ብቻ ይዞ ወጣ?

፩. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እሞታለሁ፤ እሰቀላለሁ” ባለ ጊዜ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “አቤቱ ይህ አይሁንብህ፤ ከቶም አይድረስብህ” ብሎ ተቃውሞት ነበርና አብ በደመና ሆኖ “የምወደው፣ በእርሱም ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” የሚል ቃል ተነግሯቸዋልና ይህ ለአንተ አይገባም አትበሉት፤ አትቃወሙት” ለማለት፡፡ (ማቴ. ፲፯፥፭-፮)

. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን “እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?” ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎት ነበርና አሁንም አብ “እመለክበት ዘንድ ለተዋሕዶ የመረጥኩት የምወደው ልጄ ይህ ነው” ብሎ ለማረጋገጥ፡፡

. ለፍቅሩ ስለሚሳሱ ነው፡፡  

. በይሁዳ ምክንያት ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አሥራ አንዱን ሐዋርያት ወደ ተራራ ይዞ ይሁዳን ትቶ ቢወጣ ከምሥጢር ቢለየኝ በሞቱ ገባሁበት እንዳይል ነው፡፡ ታዲያ በይሁዳ ምክንያት ስምንቱ ሐዋርያት ለምን ተከለከሉ ቢሉ፡- አልተከለከሉም፡፡ በርእሰ ደብር (በተራራው አናት) ለሦስቱ ደቀ መዛሙርት የተገለጸው ምስጢር በእግረ ደብር (በተራራው ግርጌ) ለነበሩት ስምንቱ ደቀ መዛሙርት ተገልጦላቸዋል፡፡

ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን፣ ከሙታን ሙሴን ለምን አመጣቸው?

፩. ሊቀ ነቢያት ሙሴ እግዚአብሔርን፡- “አሁንም በፊትህ ሞገስን አግኝቼ እንደሆነ ዐውቅህ ዘንድ በፊትህም ሞገስን አገኝ ዘንድ ይህም ትልቅ ሕዝብ ሕዝብህ እንደሆነ ዐውቅ ተገለጥልኝ፡፡ … ሰው አይቶኝ አይድንምና ፊቴን ማየት አይቻልህም፡፡ …እስካልፍም ድረስ እጄን በላይህ እጋርዳለሁ፡፡ እጄንም ፈቀቅ አደርጋለሁ፤ በዚያ ጊዜ ጀርባዬን ታያለህ፣ ፊቴ ግን ለአንተ አይታይም “ብሎት ነበር (ዘጸ. ፴፫፥፲፫-፳፫)፡፡ የዚህ ኃይለ ቃል ትርጓሜና ሐተታ በደብረ ታቦር ተፈጽሟል፡፡

፪. ልዑል እግዚአብሔር ነቢዩ ኤልያስን፡- “አንተ በኋለኛው ዘመን ምስክር ትሆነኛለህ” ብሎት ነበር፡፡ ይኸውም ኃይለ ቃል ኤልያስ ከብሔረ ሕያዋን መጥቶ “የእኔን የኤልያስን ጌታ ማን ኤልያስ ነው ይልሃል? እግዚአ ኤልያስ፤ አምላከ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ” ሲል በደብረ ታቦር ተፈጸመ፡፡ ታያለህ የተባለው ሙሴም አየ፣ ትመሰክራለህ የተባለው ኤልያስም መሰከረ፡፡

፫. በፊልጶስ ቂሳርያ ጌታ ሐዋርያትን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደሆነ ይሉታል?” ብሎ በጠየቃቸው ጥያቄ ሲመልሱ “ሙሴ ነው ይሉሃል ፤ እንዲሁም የኃይል ሥራህን ተመልክተው ኤልያስ ነው ይሉሃል” ብለው ነበርና ሙሴን ከመቃብር ፤ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ እግዚአ ሙሴ ፤ አምላከ ሙሴ ፤ እግዚአ ኤልያስ ፤ አምላከ ኤልያስ መሆኑን ለማስመስከር፡፡

፬. አይሁድ ፈሪሳውያን ጌታን እንደ ሕግ ተላላፊና የእግዚአብሔርን ክብር ለራሱ የሚወስድ አድርገው ያስቡት ስለ ነበረ (ዮሐ. ፱፥፲፮፤ ፲፥፴፫) ሕግን የሰጣቸው ሙሴንና ለሕገ እግዚአብሔር ቀናተኛ የነበረው ኤልያስን አምጥቶ ሕግ አፍራሽ አለመሆኑን የእግዚአብሔር ተቃዋሚም አለመሆኑን ለማስረገጥ፡፡

፭. የሐዋርያቱን የወደፊት አገልግሎት ሲነግራቸው፡፡ ይኸውም ሙሴ እና ኤልያስ ለሕዝበ እስራኤል በጣም ታማኝ እንደነበሩ ሁሉ እነርሱም ለሚያገለግሉት ሕዝብ ታማኝ እረኞች እንዲሆኑ፡፡ ምክንያቱም ውጊያቸው እንደ ሙሴ ከፈርዖን እንደ ኤልያስም ከአክዓብ ጋር ሳይሆን ከክፋት መናፍስት ጋር ነውና፡፡

ከዚህ በኋላ ጴጥሮስ “ጌታ ሆይ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው” ሲል ተደምጧል፡፡ ይህም የተለያዩ ትርጉሞች አሉት፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታ ሆይ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ማለቱ “አንተ እያበላኸን እየፈወስከን፣ ሙሴ እነዚህ መከራ ያደርሱብኛል፣ ይገድሉኛል ያልካቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያን እንዳይመጡ በደመና እየጋረደ፣ ቢመጡም አልያስ እሳት እያዘነመ እያባረራቸው በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ሲሆን ምሥጢራዊው መልእክቱ ግን “የኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት በሚታመንበት፣ ወልድ ዋሕድ በምትለው ሃይማኖት መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ ሰይጣን ድል በተደረገባት በታቦር ተራራ ምሳሌም በምትሆን በወንጌል ሕይወት፣ አንድም በቤተ ክርስቲያን መኖር ለእኛ መልካም ነው” ማለቱ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጉባኤ-ቃና መጽሔት-ነሐሴ-2016-ዓ.ም

ጉባኤ-ቃና መጽሔት-ነሐሴ-2016-ዓ.ም

“የክርስቶስን ሕግ ፈጽሙ” (ገላ. ፮፥፪)

“የክርስቶስን ሕግ ፈጽሙ” (ገላ.፥፪)

የክርስቶስ ሕግ ምንድን ነው? መልሱ ፍቅር ነው፡፡ “ባልንጀራውን የሚወድ በባልንጀራው ላይ ክፉ ሥራ አይሠራም፤ ስለዚህ ፍቅር የሕግ ፍጻሜ ነው፡፡” እንዲል (ሮሜ፲፫፥፲) በፍቅር ሕይወት መመላለስ እንዲገባን መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምረናል፡፡ ፍቅር የሕግ ሁሉ መሠረት ነውና “ፍቅራችሁ ያለ ግብዝነት ይሁን፤ ከክፉ ራቁ፤ በጎውንም ያዙ፤ ለጽድቅ አድሉ፤ እርስ በርሳችሁ በወንድማማችነት መዋደድ ተዋደዱ፣ የምትራሩም ሁኑ፤ እርስ በርሳችሁ ተከባበሩ” በማለት እግዚአብሔር በቅዱስ ጳውሎስ ላይ አድሮ ይመክረናል፡፡

አንድ ሰው ከሌላው ጋር በየዕለቱ በሚያደርገው ግንኙነት ሊመራበት የሚገባ፤ በመተሳሰብ ላይ የተመሠረተ ልባዊ መዋደድና ጥልቅ መንፈሳዊ ጸጋ ነው ፍቅር። በሰዎች መካከል በሚኖረው መልካም ግንኙነት የተነሣ አንዱ ለሌላው የሚያደርገው መልካም ነገር ሁሉ ከፍቅር የሚመነጭ ነው። ይህም በእግዚአብሔርና በሰው ዘንድ ትልቅ ዋጋን ያስገኛል፡፡ በዕለት ተዕለት ግንኙነት ለተራበ ማብላት፣ ለተጠማ ማጠጣት፣ ለተቸገረ መርዳት፣ ያዘነን ማጽናናት ይህን የመሰለውን መልካም ምግባር ሁሉ ሰው ለሰው ካለው ፍቅር የተነሣ የሚያደርገው ነው። በዚህ መሰል ተግባር ለሌሎች መልካም ያደረጉትን ሁሉ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለፍርድ በሚመጣ ጊዜ በፍጹም ፍቅር የሚወጡ የሚወርዱትን “እናንተ የአባቴ ቡሩካን፤ ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ትወርሱ ዘንድ ኑ፡፡ … እውነት እላችኋለሁ በእኔ ካመኑ ከእነዚህ ከታናናሾች ወንድሞቼ ለአንዱ ያደረጋችሁትን ከሁሉ ለእኔ አደረጋችሁት” በማለት መንግሥቱን እንደሚያወርሰን በወንጌል ተናግሯል። (ማቴ. ፳፭፥፴፭-፴፮)

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ስለ ፍቅር ሲገልጽ “እግዚአብሔር ፍቅር ነው፤ በፍቅር የሚኖርም ከእግዚአብሔር ጋር ይኖራል፤ እግዚአብሔርም ከእርሱ ጋር ይኖራል” ይለናል፡፡ (፩ኛዮሐ. ፬፥፲፮) ሰውን መውደድና ሰውን መርዳትም ፍቅር ነውና ከፍቅር አምላክ ከእግዚአብሔር ዘንድ ሰማያዊ ዋጋን ያስገኛል። ቅዱስ ጳውሎስ “እንግዲያስ ጊዜ ካገኘን ዘንድ ለሰው ሁሉ መልካም እናድርግ” ያለው በፍቅር የሚደረግ መልካም ነገር ሁሉ የሚያስገኘውን መንፈሳዊ ዋጋ በሚገባ ስለተረዳ ነው፡፡ (ገላ. ፮፥፲)። ፍቅር ለሰው መልካም በመሥራት የሰውን ድካሙን ሳይቀር በመሸፈን የሚገለጥ መልካም ተግባር ነው። ከዚህ የሚበልጥ ምንም የለምና በፍቅር እንመላለስ፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞት የማይስማማው ሲሆን መዋቲ ሥጋን ተዋሕዶ ከጽኑ ፍቅሩ የተነሣ አዳምና ልጆቹን ያድን ዘንድ በመስቀል ላይ ውሎ ሞትን በሞቱ ገድሎ ድኅነትን የሰጠን እስከ መስቀል በተከፈለ ዋጋ ነው፡፡ ለሰው ልጆች ሁሉ በመስቀል ላይ ፍቅሩን ገለጸ፣ እስከ ሞትም አደረሰው፡፡ መቃብር ውጦም አላስቀረውም፤ መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል በሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፣ ዲያብሎስንም አስወገደው፣ በትንሣኤው ትንሣኤውን አበሠረን፡፡ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ምን አለ?! ለዚህ ነው ፍቅር የሕግ ሁሉ ፍጻሜ ነው የምንለው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ የፍቅርን ኃያልነት ሲገልጽ “ፍቅር ያስታግሳል፣ ፍቅር ያስተዛዝናል፣ ፍቅር አያቀናናም፣ ፍቅር አያስመካም፣ ፍቅር ልቡናን አያስታብይም፡፡ ብቻዬን ይድላኝ አያሰኝም፣ አያበሳጭም፣ ክፉ ነገርንም አያሳስብም፡፡ …” በማለት ይነግረናል። (፩ኛቆሮ. ፲፫፥፬-፯) በአጠቃላይ ሁሉንም በመውደድ፣ በጎ ምግባርንም በመፈጸም እንደ እግዚአብሔር ቃል በፍቅር መኖር ስንችል የሕሊና ዕረፍትን እናገኛለን፣ በመንፈሳዊ ሕይወታችንም እናድጋለን፡፡

በክርስትና ሕይወት ዕድገት እያመጣን ስንሄድ ዲያብሎስ ደግሞ በእርምጃን ሁሉ ፈተናን በማዘጋጀት ሊጥለን የሚችለውን ሁሉ ያደርጋል፡፡ በተለይም በወጣትነት ዘመናችን ሁሉንም ካልሞከርኩ፣ ካላየሁ፣ ካልዳሰስኩ የምንልበት ጊዜ በመሆኑ ሥጋዊ ፍላጎታችንም ስለሚያይል ኃጢአትን ለመሥራት እንፈጥናለን፡፡ ነገር ግን ይህንን ሥጋዊ ፍላጎትና ስሜት መግታት የምንችለው ወደ እግዚአብሔር በመቅረብና ለሕግጋቱ በመገዛት ዲያብሎስን ድል መንሣት ስንችል ነው፡፡ ጠቢቡ በወጣትነት ዘመን ፈጣሪን ማሰብ ተገቢ መሆኑን ሲያስረዳ “በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን ዐስብ” ይላል፡፡ (መክ. ፲፪፥፩)

ዲያብሎስ በወጣትነት ድል ሊያደርገን የተለያዩ ማታለያዎችን በማቅረብ ራሳችንን ብቻ እንድንወድ ይፈትነናል፡፡ ነገር ግን በጾም በመጸሎት፣ መልካም ምግባራትን በመፈጸም ልናርቀው ይገባል፡፡ ሌላውን ስንወድ እግዚአብሔርን እንወዳለን፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ነውን? ሐዘን ነውን? ስደት ነውን? ራብ ነውን? መራቆት ነውን? ጭንቀት ነውን? ሾተል ነውን? … ከክርስቶስ ፍቅር የሚለየን የለም” (ሮሜ ፰፥፴፭-፴፰) በማለት ክርስቲያን ስንሆን እነዚህ ፈተናዎች እንደሚገጥሙን፣ ነገር ግን የፍቅር ሁሉ ምንጭ ከሆነው ክርስቶስ ጋር ተጣብቀናልና በድል እንወጣዋለን፡፡ እግዚአብሔር ያለው ሁለም ነገር አለውና፡፡ 

እግዚአብሔር በአምላክነቱ ቀናተኛ አምላክ ነው፡፡ እርሱን መውደድ፣ እንዲሁም ሰውን ሁሉ መውደድ እንደሚገባን አስተምሮናል፡፡ የክርስትና መሠረትም በዚህ ላይ የተመሠረተ ነው። “አምላክህን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ነፍስህ፣ በፍጹም ኃይልህ ውደደው፤ ታላቂቱና የመጀመሪያይቱ ትእዛዝ ይህች ናት፡፡ የምትመስላትም ሁለተኛይቱም ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የምትለው ናት” እንዲል፡፡ (ማቴ፳፪፥፴፯-፴፰) ራሳችንን የምንወደውን ያህል አጠገባችን ያለውን ባልንጀራችንን የምንወድ ከሆነ ከእግዚአብሔር ጋር ሕብረት ይኖረናል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ጠላታችንን እንወድ ዘንድም ታዘናል፡፡ “ባልንጀራህን ውደድ፣ ጠላትህንም ጥላ የተባለውን ሰምታችኋል፡፡ እኔ ግን እላችኋለሁ፤ ጠላታችሁን ውደዱ፤ የሚረግሟችሁንም መርቁ …” ተብለናል፡፡ (ማቴ.፭፥፵፫) ይህንንም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አይሁድ በጠላትነት ተነሥተው አሳደውታል፣ ገርፈውታል፣ ምራቅ ተፍተውበታል፣ … ጠላቶቹ ሲሆኑ በጭካኔ በመስቀል ላይ ሰቅለውት እንኳን “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” ሲል በፍቅር ዐይኖቹ እየተመለከተ ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ ይቅርታን ለምኖላቸዋል፡፡ (ሉቃ፳፫፥፴፬)

እኛስ እንኳን ጠላቶቻችን ወዳጆቻችንን እንወድ ይሆን? በአፍ ከመናገር አልፈን ሁሉንም የመውደድ ግዴታ እንዳለብን ካልተረዳን በተግባርም ካልገለጥነው አጠገባችን በአካል የምናየውን ወዳጃችንን ሳንወድ የማናየውን እግዚአብሔርን እንወዳለን ማለት ራስን ማታለል ነው፡፡ “እግዚአብሔርን እወደዋለሁ የሚል ወንድሙን ግን የሚጠላ ሐሰተኛ ነው፤ የሚያየውን ወንድሙን የማይወድ ግን የማያየውን እግዚአብሔርን እንደምን ሊወደው ይችላል?” ይለናል የእግዚአብሔር ቃል፡፡ (፩ኛዮሐ. ፬፥፳) ነገር ግን እርስ በርስ የምንዋደድና በፍቅር የምንኖር ከሆነ እግዚአብሔር አድሮብን ይኖራል፡፡ “ወንድሞች ሆይ እግዚአብሔር ይህን ያህል ከወደደን እኛም እርስ በርሳችን ከተዋደድን እግዚአብሔር አድሮብን ይኖራል፤ ፍቅሩም በእኛ ፍጹም ይሆናል፡፡” (፩ዮሐ.፬፥፲፩-፲፪)

ስለ ኃጢአታችን ከገነት የተባረርነውን አዳምና ልጆቹን ያድነን ዘንድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስት ዽንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ፣ በምድር ላይ ተመላልሶ በመስቀል ላይ ያለ በደሉ የአዳምን በደል ይሽር ዘንድ ተሰቅሎ፣ ሲዖልን በርብሮ ዲያብስን ድል ነሥቶ ያድነን ዘንድ እስከ መስቀል የታመነ አምላክ ነው፡፡ በሞቱ ሞትን ገድሎ በትንሣኤው ትንሣኤአችንን አወጀልን፡፡ ይህ ሁሉ ለሰው ልጆች የተከፈለ ዋጋ ነው፡፡ “ስለ ወዳጆቹ ሕይወቱን አሳልፎ የሚሰጥ ሰው ያለ እንደሆነ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም፡፡” እንዲል፡፡ (ዮሐ. ፲፭፥፲፫)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ መልእክቱ ለመንፈሳዊ ነጻነት የተጠራንበት የክርስትና እምነታችንን በተለያዩ የሥጋ ፈቃዳትና ፈተናዎች ተሰናክለን እንዳንወድቅ እና ፍሬ አልባ እንዳንሆን ሲያስጠነቅቀንም “ወንድሞች ሆይ እናንተ ለአርነት ተጠርታችኃልና፤ ብቻ አርነታችሁ ለሥጋ ምክንያት አይስጥ፤ ነገር ግን በፍቅር እርስ በርሳችሁ እንደ ባሪያዎች ሁኑ” በማለት ራስን ዝቅ በማድረግና በፍቅር በመመላለስ የእግዚአብሔርን ሕግ ልንፈጽም ይገባል፡፡ (ገላ. ፭፥፲፫)

የሕግ ሁሉ ፍጻሜው ፍቅር ነውና በፍቅር ተመላለሰን፣ ንስሓ ገብተን፣ የመንግሥቱ ወራሾች ያደርገን ዘንድ የአምላክችን ቅዱስ እግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን፡፡ አሜን፡፡

ሰሙነ ሕማማት

ክፍል ሦስት

. ዕለተ ረቡዕ

በሰሙነ ሕማማት ዕለተ ረቡዕ የሚከተሉት ሦስት ነገሮች ተፈጽመዋል፡-

  • የካህናት አለቆች፣ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ ተማክረዋል፤
  • ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ ማርያም እንተ ዕፍረት ስለ ኃጢአቷ ተጸጽታ ዕንባዋን እያፈሰሰች ውድ ሽቱ ቀብታዋለች፤
  • ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያንና ከካህናት አለቆች ዘንድ ሠላሳ ብር ለመቀበል ተማክሯል (ተስማምቷል)፡፡

 . ምክረ አይሁድ፡ 

የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሹማምንት በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስን ለመያዝና ለመግደል በቀያፋ የሚመራው ሸንጐ በአጠቃላይ ሰባ ሁለት አባላት ነበሩት፡፡ በዕለቱ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት ይዘው እንደሚገድሉት አይሁድ በዚህ ሸንጎ መክረዋል፡፡

ከዳተኛው ይሁዳም ጸሐፍት ፈሪሳውያንና የካህናት አለቆች በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ላይ የነበራቸውን ጥላቻ ያውቅ ስለነበር “ምን ትሰጡኛላችሁ? እኔም አሳልፌ እሰጣችኋለሁ” በማለት ጌታችንን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ተስማምቷል (ማቴ. ፳፮፥፲፭)፡፡

በዚህም  መሠረት ይህቺ ዕለት የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ፈሪሳውያን ጌታ ኢየሱስን እንዴት መያዝ እንዳለባቸው ምክር የመከሩበት ምክራቸውንም ያጸኑበትና ሰቅለው ይገድሉት ዘንድ የወሰኑባት ቀን በመሆኗ የአይሁድ የምክር ቀን ተብላ ትጠራለች፡፡ ይሁን እንጂ በዚሁ ምክራቸው ወቅት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስን እንዴት አድርገው እንደሚይዙት በጣም ይጨነቁ ነበር፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ወቅቱ የፋሲካ በዓላቸውን የሚያከብሩበት ወቅት በመሆኑ በጌታችን ትምህርት የተማረኩ ብዙ ሕዝብ ትምህርቱን ያደንቁ ስለነበር ሁከት እንዳይፈጠር ከመፍራታቸው የተነሣ ነው፡፡ በዚህ ጭንቀትም ሳሉ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል አንዱ የሆነው የአስቆሮቱ ይሁዳ በመካከላቸው ተገኝቶ ጌታ ኢየሱስን እርሱ በመሳም አሳልፎ እንደሚሰጣቸው፤ ለዚህ ተግባሩም ሠላሳ ብር ወረታውን እንዲከፍሉት ከእነርሱ ጋር በመስማማቱና የምክራቸው ተባባሪ በመሆኑ ጭንቀታቸውን አስወግዶላቸዋል፡፡ (ማር. ፳፮፥፩-፭ ፤ ፳፮፥፲፬-፲፮ ፤ ማር. ፲፬፥፩-፲፩ ፤ ሉቃ. ፳፪፥፩)

. የመልካም መዓዛ ቀን፡

ዕለተ ረቡዕ ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ተቀምጦ ሳለ በመላ ዘመንዋ ራስዋን ለኃጢአት በማስገዛት በዝሙት ትኖር የነበረችው ማርያም እንተ ዕፍረት ኃጢአትን ይቅር የሚል መልካም መዓዛ ያለው አምላክ መጣ ስትል ውድ የሆነ ዋጋ ያለው ወይም የሦስት መቶ ዲናር ሽቱን ገዝታ ወደ እርሱ በመምጣትና በራሱ ላይ በማርከፍከፍ ስለቀባችው የመልካም መዓዛ ቀንም ትባላለች፡፡ በዚህም ምክንያት ከኃጢአትዋ የተነሣ መልካም መዓዛ ያልነበራት ማርያም እንተ ዕፍረት በዚህ በጎ ተግባርዋ መልካም መዓዛ ያላት ሆና ወደ ቤትዋ ተመልሳለች፡፡ (ማቴ. ፳፮፥፮ ፤ ዮሐ. ፲፪፥፩-፰)

. የዕንባ ቀን፡

ማርያም እንተ ዕፍረት በጌታችን እግር ላይ ተደፍታ መላ ኃጢአቷን ይቅር እንዲላት በዕንባዋ እግሩን እያጠበች፣ በፀጉሯም እግሩን እያበሰች ስለ ኃጢአቷ ሥርየት ተማጽናዋለችና የዕንባ ቀን ትባላለች፡፡ (ማቴ. ፳፮፥፮-፲፫ ፤ ማር. ፲፬፥፫-፱ ፤ ዮሐ. ፲፪፥፩-፰)

የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተምር በነበረበት ወቅት ከምእመናን ለሚገባው ገንዘብ ሰብሳቢ (ዐቃቤ ንዋይ) ነበር፡፡ ከሚሰበሰበው ሙዳየ ምጽዋት ለግል ጥቅሙ እየቀረጠ የማስቀረት የእጅ አመል ነበረበት፡፡ ይሁዳ ፍቅረ ንዋይ እንደሚያጠቃው ድብቅ አመሉ ጎልቶ የወጣው ጌታችን በለምጻሙ በስምዖን ቤት ሳለ አንዲት ሴት ዋጋው ውድ የነ ሽቱ በቀባችው ጊዜ ነው፡፡ በዚያች ዕለት ይሁዳ የተቃውሞ ድምፅ አሰምቶ ነበር፡፡

“ይህ ሽቱ ተሽጦ ለድሆች ቢሰጥ መልካም ነበር” አለ፡፡ ሽቱ ሲሸጥ የሚያገኘው ጥቅም አለ፤ ሽቶው በጌታችን እግር ሥር ከፈሰሰ ለእርሱ የሚተርፈው የለም፡፡ ይሁዳ ተቆርቋሪ መስሎ ያቀረበው አሳብ ተቀባይነት በማጣቱም ማኩረፊያ ያገኘ መስሎት በቀጥታ ከካህናት አለቆች ዘንድ ሔዶ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሠላሳ ብር ለመሸጥ ተዋዋለ፡፡ (ማቴ. ፳፮፥፫-፲፮፤ ማር. ፲፬፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፪፥፩፮)፡፡

ክርስቲያን ነን በማለት የክርስትናውን ስም ብቻ በመያዝ እምነታቸውን፣ በገንዘብ የሚለውጡ ሰዎች ዛሬም እንደ ይሁዳ ጌታችንን እየሸጡት እንደ ሆነ ሊገነዘቡት ይገባል፡፡ ለድሆች መመጽወት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ዳሩ ግን በድሆች ስም የሰውን ገንዘብ ለግል ጥቅም ማዋል እጅግ የከፋ ኃጢአት ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለገንዘብ ብለው ድሆችን ለረኃብ ለችግር ባልንጀራቸውን ለመከራ እና ለሞት አሳልፈው ሲሰጡ ምንም አይጸጽታቸውም፡፡ እውነተኛ ክርስቲያኖች ግን ሕይወታችንን ለገንዘብ ፍቅር ሳይሆን ለእምነታችንና ለባልንጀራችን አሳልፈን መስጠት ይኖርብናል፡፡ በፍቅረ ንዋይ ተጠምደን ሰዎችን አሳልፎ በመስጠት ለአይሁዳውያን ሸንጐ ምቹ ሆነን መገኘት እንደማይገባ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሰሙነ ሕማማት

ክፍል ሁለት

. ዕለተ ሠሉስ

. የጥያቄ ቀን፡ ከሰሙነ ሕማማት ዕለታት ውስጥ ዕለተ ሠሉስ የጥያቄ ቀን በመባል ይታወቃል፤ ምክንያቱም ሹመትን ወይም ሥልጣንን ለሰው ልጅ የሰጠ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰኞ ዕለት አንጽሖተ ቤተ መቅደስን ከፈጸመ በኋላ በዚህች ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ ሲያስተምር የካህናት አለቆችና የሕዝቡ ሽማግሌዎች ወደ እርሱ መጥተው “በማን ሥልጣን ይህ ታደርጋለህ? ይህንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ?” አሉት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ እኔም አንዲት ቃል እጠይቃችኋለሁ፣ የነገራችሁኝ እንደሆነ እኔም በምን ሥልጣን ይህን እንደማደርግ እነግራችኋለሁ” አላቸው፡፡ ጌታችንም ጥያቄውን ይመልሱለት ዘንድ “የዮሐንስ ጥምቀቱ ከየት ነው? ከሰማይ ነውን? ወይስ ከሰው?ሲል ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም እርስ በርሳቸው ተነጋግረው እንዲህ አሉ “ከሰማይ ነው ብንለው እንኪያ ለምን አላመናችሁትም? ይለናል፡፡ ከሰው ነው ብንለውም ዮሐንስን ሁሉም እንደ ነቢይ ያዩታልና ሕዝቡን እንፈራቸዋለን ተባባሉ፡፡ በመጨረሻም መልስ መስጠት ስላልቻሉ “ከወዴት እንደሆነ አናውቅም” ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም “እንኪያስ እኔም በምን ሥልጣን ይህን እንደማደርግ አልነግራችሁም” አላቸው፡፡ ይህን ጥያቄ መጠየቃቸውም እርሱ የሚያደርጋቸውን ተግባራት ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተውት አልነበረም፤ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ ነበር እንጂ፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፳፫-፳፯ ፤ ማር. ፲፩፥፳፯-፴፫፣ ሉቃ. ፳፥፩-፰) በዚህም ምክንያት የሰሙነ ሕማማት ማክሰኞ የጥያቄ ቀን ይባላል፡፡

. የትምህርት ቀን፡ ይህቺ ዕለት ዕለተ ትምህርት ወይም የትምህርት ቀን በመባልም ትጠራለች፡፡ ጌታችን በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት በማስተማር የተሰጠው ስያሜ ሲሆን ይኸውም ከሃይማኖት የራቁትን፣ ከፍቅረ እግዚአብሔር የተለዩትን አስተምሮ ማቅረብና መክሮ መመለስ እንደሚገባን ሲገልጽልን ነው፡፡

በዚህም ትምህርቱ ሁለት ወንድማማቾችን አባታቸው ወደ ወይን ቦታ ሄደው ይሠሩ ዘንድ እንደጠየቃቸው፤ የመጀመሪያው እምቢ ቢልም ተጸጽቶ ሊሠራ መሄዱን፤ ሁለተኛውም እሺ ብሎ ነገር ግን ቃሉን አጥፎ ሳይሄድ መቅረቱን ነገራቸው፡፡ እርሱም ትምህርቱን ከነገራቸው በኋላ አስተምሮ ብቻ አልተዋቸውም፤ ጥያቄውን አስከትሏል፡፡ “እንግዲህ ከሁለቱ የአባቱን ፈቃድ የፈጸመ ማንኛው ነው?” ሲል ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም “ፊተኛው ነዋ” አሉት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ ሲል ገሠጻቸው፡- “እውነት እላችኋለሁ፤ ቀራጮችና አመንዝሮች ወደ እግዚአብሔር መንግሥጥ በመግባት ይቀድሟችኋል፡፡ ዮሐንስ ወደ እናንተ በጽድቅ ጎዳና መጣ፤ አላመናችሁበትም፣ ቀራጮችና አመንዝሮች ግን አመኑበት፤ እናንተም በኋላ በእርሱ ለማምነን አይታችሁ እንኳ ንስሓ አልገባችሁም” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፳፰ ፤ ፳፭፥፵፮ ፤ ማር. ፲፪፥፪ ፤ ፲፫፥፴፯ ፤ ሉቃ. ፳፥፱ ፤ ፳፩፥፴፰)

 ሌላው በዚሁ ቀን በምሳሌ ያስተማረው ትምህርት ስለ ወይን እና ወይኑን የተከለው ባለቤት ድካም የተመለከተ ነበር፡፡ “ሌላ ምሳሌ ስሙ፤ ባለቤት ሰው ወይንን ተከለ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፤ መጭመቂያም አስቆፈረለት፤ ግንብንም ሠራለት፤ ለገባሮችም ሰጥቷቸው ሄደ፡፡ የሚያፈራበት ወራት በደረስ ጊዜም ከወይኑ ፍሬ ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮቹን ወደ ገባሮቹ ላከ፡፡ ገባሮቹም አገልጋዮቹን ይዘው አንዱን በበትር ደበደቡት፣ አንዱንም ገደሉት፣ ሌላውንም በድንጋይ መቱት፡፡” በማለት አስረዳቸው፡፡ በዚህም በብቻ አላበቃም ሌሎችን ከዚህ በፊት ከላካቸው አገልጋዮች ቁጥር በላይ ወደ ገባሮቹ ሰደዳቸው፡፡ ነገር ግን ገባሮቹ የተላኩትን አገልጋዮች ደብድበው አባረሯቸው፡፡

 ባለ ወይኑ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ ልጄን ያከብሩትና ይፈሩት ይሆናል ብሎ አንድ ልጁን ከወይኑ ያመጣለት ዘንድ ወደ ገባሮቹ ላከው፡፡ ገባሮቹም ልጁን ባዩት ጊዜ እርስ በርሳቸው “እነሆ ወራሹ ይህ ነው፤ ኑ እንግደለውና ርስቱን እንውረስ ተባባሉ፡፡ ይዘውም ከወይኑ ቦታ ውጭ አውጥተው ገደሉት፡፡ እንግዲህ የወይኑ ቦታ ባለቤት በመጣ ጊዜ እነዚህ ገባሮች ምን ያደርጋቸዋል?” ሲል ጠየቃቸው፡፡

 የካህናት አለቆችንና የሕዝቡ ሽማግሌዎችም “ክፉዎችን በክፉ ያጠፋቸዋል፤ ወይኑንም በየጊዜው ፍሬውን ለሚሰጡት ለሌሎች ገባሮች ይሰጣል” አሉት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ አላቸው”… ግንበኞች የናቁአት ድንጋይ የማዕዘን ራስ ሆነች፡፡ … ስለዚህ እላችኋለሁ፡- የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ ትወሰዳለች፤ ፍሬዋንም ለሚያደርጉ ለአሕዘብ ትሰጣለች፡፡ በዚያችም ድንጋይ ላይ የሚወድቅ ይቀጠቀጣል፡፡፣ በላዩ የሚወድቅበትንም ትፈጨዋለች” የካህናት አለቆችና ጸሐፍት ፈሪሳውያንም ይህ ስለ እነርሱ የተነገረ መሆኑን ዐወቁ፡፡

ለሦስተኛ ጊዜም ለልጁ ሠርግ ስለ አደረገው ንጉሥ በምሳሌ አስተማራቸው፡፡ እነርሱ ግን ያስተማራቸውን ትምህርት ተረድተው ወደ ንስሓ ከመመለስ ይልቅ ጌታችን መድኃነኒታችን ኢያሱስ ክርስቶስን በአነጋገሩ ያጠምዱትና ይይዙት ዘንድ ተማከሩ፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፳፫-፵፭ ፤ ፳፪፥፩-፳፪)፡፡

ይቆየን

“መኑ ውእቱ ገብር ኄር፤ ታማኝ አገልጋይ ማነው?” (ማቴ. ፳፬፥፵፭)

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ መሠረት የዐቢይ ጾም ስድስተኛው ሳምንት ገብር ኄር ይባላል፡፡ ሰያሜውንም የሰጠው ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በሆነው ጾመ ድጓ በተባለው መጽሐፍ የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህም መሠረት በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብር ኄር ወይም ታማኝ አገልጋይ ላይ ትኩረት ያደርጋል፡፡

ይህንንም ወንጌላው ቅዱስ ማቴዎስ እንዲህ እያለ ይገልጸዋል፡፡ “መንገድ እንደሚሄድ አገልጋዮቹንም ጠርቶ ሊያተርፉበት ገንዘቡን እንደሰጣቸው ሰው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ችሎታው ለአንዱ አምስት፣ ለአንድ አምስት፣ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ያ አምስት መክሊት የተቀበለውም ሄደ፤ ነግዶም ሌላ አምስት መክሊት አተረፈ፡፡ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ወርቅ ቀበረ፡፡” (ማቴ. ፳፭፥፲፬-፲፰)

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ይቆጣጠራቸው ዘንድ ተመልሶ መጣ፡፡ “ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር ላይ እምነት ያገኝ ይሆን?” እንዲል በእነዚህ አገልጋዮች አንጻር ምእመናን ለእግዚአብሔር ያላቸውን እምነትና ታማኝነት፣ ታምኖም መኖር ምን ያህል እንደሆነ የሚያመለክት ነው፡፡ (ሉቃ .፲፰፥፰)

አገልጋዮቹም ከጌታቸው የተቀበሉትን መክሊትና ያተረፉትን ይዘው በተራ ቀረቡ፡፡  በቅድሚያም አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና፡- “አቤቱ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት አተረፍሁ፤ ብሎ አምስት መክሊት አስረከበ፡፡ ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም መጥቶ፡- አቤቱ ሁለት መክሊትን ሰጥተኸኝ አልነበረምን? እነሆ ሌላ ሁለት መክሊትን አተረፍሁ አለ፡፡ ጌታውም፡- መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡” ሁለቱም የተሰጣቸውን መክሊት ተጠቅመው ወጥተው ወርደው ሠርተውና አትርፈው ተገኝተዋልና ያገኙትንም ይዘው በመቅረብ ከጌታቸው ዘንድ ሞገስና ክብርን አግኝተዋል፡፡

ጌታው ሠርቶ፣ አገልግሎ ያተርፍበት ዘንድ አንድ መክሊት የተሰጠው አገልጋ ግን ከሁለቱ በተለየ መንገድ ወደ ጌታው ቀረበ፡፡  “አንድ መክሊት የተቀበለውም መጣና እንዲህ አለ፡- አቤቱ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሄድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤ እንግዲህ እነሆ መክሊትህ” አለው፡፡  ጌታውም መልሶ አለው፡- “አንተ ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እኔ ካልዘራሁበት የማጭድ ካልበተንሁበት የምሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንሁ ታውቃለህ? ገንዘቤን ለለዋጮች መስጠት በተገባህ ነበር፤ እኔም ራሴ መጥቼ ገንዘቤን ከትርፉ ጋር በወሰድሁ ነበር፡፡ የቆሙትንም እንዲህ አላቸው፡- ይህን መክሊት ከእርሱ ተቀብላችሁ ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ሁሉ ይሰጡታልና ይጨምሩለታልም፡ ለሌለው ግን ያንኑ ያለውን ይወስዱበታል፡፡ ክፉውን አገልጋይ ግን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት በውጭ ወደአለ ጨለማ አውጡት፡፡” (ማቴ. ፳፭፥፲፬-፴) አለ፡፡

ባዕለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፡፡ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው፤ መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት በዕለተ ምጽአት ለሁሉም በአገለገለው አገልግሎት ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ የሚያሳይ ነው፡፡

ያገለገሉትና ታምነው የተገኙት ወደ ጌታህ ደስታ ግባ ማለቱ ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን እንደሚወርሱ፤ ሰነፎች ደግሞ ጥርስ ማፋጨት፣ ስቃይ፣ ጽኑዕ ጨለማ ባለበት ሲዖል መውረዳቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

ነቢያት፣ ጻድቃን ሠማዕታት፣ ቅዱሳን በታማኝ አገልግሎታቸው ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ሊቀ ነቢያት ሙሴ፣ ዮሴፍ፣ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት፣ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ቅዱስ ጳውሎስን ማንሣት የምንችል ሲሆን፤ ለጌታቸው ያልታመኑት ደግሞ ይሁዳ፣ ሐናንያ፣ ሰጲራ፣ የመሳሰሉት የደረሰባቸውን ጉዳት መጥቀስ ይቻላል፡፡

ለዚህ ነበር ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ አድነኝ ደግ ሰው አልቋልና፤ ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሏልና” በማለት የገለጸው፡፡ (መዝ. ፲፩፥፩) ስለዚህ ሁሉም በየአለበት የአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ “አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሀለሁ” የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል መስማት ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን መንግሥቱን እንድንወርስ፣ “ገብርኄር” እንድንባል አምላካችን ይርዳን፡፡

የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)

“መኑ ውእቱ ገብር ኄር ወምእመን ዘይረክቦ እግዚኡ በምግባረ ሠናይ ወይሰይሞ ዲበ ኲሉ ንዋዩ፡፡ ካዕበ ይቤሎ እግዚአብሔር ገብር ኄር ወምእመን ዘበውኁድ ወምእመን ዘበውኁድ ምእመነ ኮንከ ዲበ ብዙኅ እሰይመከ ባዕ ውስተ ፍሥሐሁ ለእግዚእከ፡፡

ትርጉም– “ጌታው መልካም ሲሠራ አግኝቶ በገንዘቡ ሁሉ ላይ የሚሾመው ቸርና ታማኝ አገልጋይ ማን ነው? ዳግመኛም እግዚአብሔር በታናሹ የታመንህ ደግና ታማኝ አገልጋይ ሆይ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው፡፡

 መልእክታት

የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት፡- (፪ኛጢሞ. ፲፮)

“እንግዲህ፥ ልጄ ሆይ፥ አንተ በክርስቶስ ኢየሱስ ባለው ጸጋ በርታ። ብዙ ሰዎች የመሰከሩለትን ከእኔም የሰማኸውን ሌሎችን ደግሞ ሊያስተምሩ ለሚችሉ ለታመኑ ሰዎች አደራ ስጥ። እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ወታደር ሆነህ፥ አብረኸኝ መከራ ተቀበል። የሚዘምተው ሁሉ ለጦር ያስከተተውን ደስ ያሰኝ ዘንድ ትዳር በሚገኝበት ንግድ ራሱን አያጠላልፍም። ደግሞም በጨዋታ የሚታገል ማንም ቢሆን፥ እንደሚገባ አድርጎ ባይታገል፥ የድሉን አክሊል አያገኝም። የሚደክመው ገበሬ ፍሬውን ከሚበሉት መጀመሪያ እንዲሆን ይገባዋል። …”

የሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ መልእክት፡- (፩ኛጴጥ. ፲፪)

“እንግዲህ እኔ፥ ከእነርሱ ጋር ሽማግሌ የክርስቶስም መከራ ምስክር ደግሞም ሊገለጥ ካለው ክብር ተካፋይ የሆንሁ፥ በመካከላቸው ያሉትን ሽማግሌዎች እመክራቸዋለሁ፤ በእናንተ ዘንድ ያለውን የእግዚአብሔርን መንጋ ጠብቁ፤ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በውድ እንጂ በግድ ሳይሆን፥ በበጎ ፈቃድ እንጂ መጥፎውን ረብ በመመኘት ሳይሆን ጐብኙት፤ ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ እንጂ ማኅበሮቻችሁን በኃይል አትግዙ፤ የእረኞችም አለቃ በሚገለጥበት ጊዜ የማያልፈውን የክብርን አክሊል ትቀበላላችሁ። …”

 ግብረ ሐዋርያት፡- (ሐዋ. ፱)

“እነርሱም በተሰበሰቡ ጊዜ ጌታ ሆይ፥ በዚህ ወራት ለእስራኤል መንግሥትን ትመልሳለህን? ብለው ጠየቁት። እርሱም። አብ በገዛ ሥልጣኑ ያደረገውን ወራትንና ዘመናትን ታውቁ ዘንድ ለእናንተ አልተሰጣችሁም፤ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ አለ። ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው።”

ምስባክ፡- (መዝ. ፴፱፰-፱)

ከመ እንግር ፈቃደከ መከርኩ አምላኪየ፤ ወሕግከኒ በማዕከለ ከርሥየ፤ ዜኖኩ ጽድቀከ በማኅበር ዐቢይ፡፡
ትርጉም፦ “አምላኬ ሆይ፥ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፥ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው። በታላቅ ጉባኤ ጽድቅን አወራሁ፡፡”

 ወንጌል (ማቴ. ፳፭፲፬፴፩)

“መንገድ እንደሚሄድ አገልጋዮቹንም ጠርቶ ሊያተርፉበት ገንዘቡን እንደሰጣቸው ሰው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ችሎታው ለአንዱ አምስት፣ ለአንድ አምስት፣ ለአንዱም አንድ ሰጠና ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ያ አምስት መክሊት የተቀበለውም ሄደ፤ ነግዶም ሌላ አምስት መክሊት አተረፈ፡፡ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ወርቅ ቀበረ፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ተመልሶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና፡- አቤቱ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ ሌላ አምስት አተረፍሁ፤ ብሎ አምስት መክሊት አስረከበ፡፡ ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም መጥቶ ፡- አቤቱ ሁለት መክሊትን ሰጥተኸኝ አልነበረምን? እነሆ ሌላ ሁለት መክሊትን አተረፍሁ አለ፡፡ ጌታውም፡- መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ የታመንህ ስለ ሆንህ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለውም መጣና እንዲህ አለ፡- አቤቱ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሄድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤ እንግዲህ እነሆ መክሊትህ፡፡ ጌታውም መልሶ አለው፡- አንተ ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እኔ ካልዘራሁበት የማጭድ ካልበተንሁበት የምሰበስብ ጨካኝ ሰው እንደሆንሁ ታውቃለህ? ገንዘቤን ለለዋጮች መስጠት በተገባህ ነበር፤ እኔም ራሴ መጠቼ ገንዘቤን ከትርፉ ጋር በወሰድሁ ነበር፡፡ የቆሙትንም እንዲህ አላቸው፡- ይህን መክሊት ከእርሱ ተቀብላችሁ ዐሥር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ሁሉ ይሰጡታልና ይጨምሩለታልም፡ ለሌለው ግን ያንኑ ያለውን ይወስዱበታል፡፡ ክፉውን አገልጋይ ግን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት በውጭ ወደአለ ጨለማ አውጡት፡፡”

ቅዳሴ: ዘባስልዮስ

ቅድስት

ትዕግሥት ባሳዝነው

ሰውነቴን ሳስብ በትዕቢት መዛሉን፣                                                   ሰው ከንቱ፣ ሰው መና፤ ከአምላኩ ተጣልቶ፣

ከንቱነቴን አየሁ በስስት መድከሙን፣                                               ለዲያቢሎስ ግብር፣ ለክፋት ያደረ ያልተሰጠን ሽቶ፣

እኔነቴን አየሁ ማምለኩ ገንዘብን፡፡                                                      ሲሰግድ የሚያድር ለቂም ሐውልት ሠርቶ፣

ይህን ሁሉ ሠርቼ አምላክ ላንዴ ባየው፣                                             ሲዘምር የሚያድር በጥላቻ ሰክሮ፣

እኔን ለማዳን መች ተሣነው፡፡                                                              ሲቀድስ የሚውል በመለያየት ጸንቶ፣

አምላክነቱን ረስቶ ሰው የሆነ መስሎት፣                                            ሰው ከንቱ፣ ሰው መና በትዕቢት ተውጦ፣

ዲያብሎስ ሊያስተው ቢፈትነው በትዕቢት፣                                    ሽማግሌን አሳዝኖ፣ ታላቁን አቅልሎ፣

አርባ ቀን አርባ ሌት፣                                                                         ለስስት ተገዝቶ ባለእንጀራን ክዶ፣

ጾምን አስተባብሮ በመቆም ለፀሎት፣                                                ገንዘብን የሚያመልክ ከሰውነት ወጥቶ፡፡

ዲያቢሎስ አፈረ ወጥመዱ ከሽፎበት፡፡                                               ጾሙንም በትዕቢት፣ ጸሎትን በስስት፣

አምላክ በእኒህ ኃጢያት ቢፈተንም ቅሉ፣                                         ምፅዋትን በፍቅረ ንዋይ፣

ዳሩ ለእኛ ነበር ለክርስቲያን ሁሉ፣                                                    እንዲህ ቢያታልል ወደ አምላኩ ሳያይ፣

ክርስቲያን ከተባልን ከክርስቶስ ወስደን፣                                         እርሱ ግን ይታያል ሥራውም በአዶናይ፣

ጾምንም ከጾምናት ከአምላክ ተምረን፣                                              እናም እንዲህ አልኩኝ አምላኬን ስማጸን፣

ታዲያ ለምን ይሆን ትዕቢት ያሳበጠን፣                                            ጾምህን ስንጾም ትዕቢታችን ይራቅ፣

ስስት ያጎበጠን፣ ገንዘብ ያስመለከን?                                                ጸሎትህን ስንጸልይ ትኅትናችን ይድመቅ፡፡

ጾማችንን ሳንሽር ጸሎታችን ሳንተው፣                                             አባት ሆይ ስንልህ ስስታችን ይጥፋ፣

በኃጢያት ደልበን በበደል የኖርነው፣                                               አምላካችን ስንል ፍቅርችንን አስፋ፣

ንስሓን ረግጠን ልጅነት ያጣነው፡፡                                                     ፍቅረ ነዋይም ይጥፋ፣

ሰው ከንቱ፣ ሰው መና፤ በዓለም የታለለ፣                                          በጾምህ ቀድሰን፣ በጸሎትህ አጽናን፣

በሰም ብቻ ከብሮ በግብሩ የተጣለ፣                                                   ዛሬም እንደ ጥንቱ ስንጠፋ ፈልገን፣

ሰውነቱ ከብዶት ሰው መሆን የረሳ፣                                                   አባታችን ስንል ልጆቼ ኑ በለን፣

ለዲያቢሎስ ግብር ለእርሱው እጅ የነሳ፣                                           ዛሬም ስንበድል በንስሓ ማረን፣

ጓደኛውን ክዶ አምላኩን ያስቆጣ፣                                                    በፍቅርህ አክመን፣ በቁስልህ ፈውሰን፣

የሌለውን ሽቶ ያለውንም ያጣ፡፡                                                          በሞትህ አድነን በመስቀልህ ጋርደን፣

በበደሉ ደልቦ በክፋት የኖረ፣                                                              ቅድስቷን እንቀድስ ከበደል አረቀህ ፣

ቂም በቀልን ቋጥሮ ሕጉንም የሻረ፣                                                    ጾምህን አስጀምረን,

በባልጀራው መኖር እርሱ እንቅልፍ ያጣ፣                                        ትዕቢት፣ስስት፣ ፍቅረ ንዋይ አጠፋ ከልባችን።

ከሰውነት ክብር ከሥርዓት የወጣ፡፡

ቅድስት (የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት)

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በጾመ ድጓ ድርሰቱ በዐቢይ ጾም ለሚገኙት ሳምንታት ማለትም በየሳምንቱ ለሚውሉት እሑዶች መዝሙር አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ በዚህም መሠረት እያንዳንዱ እሑድ በመዝሙሩ ስም ይጠራል። ባለፈው ሳምንት “ዘወረደ”ን እንዳቀረብን ሁሉ በዚህ ዝግጅታችን ደግሞ ሁለተኛውን ሳምንት ቅድስትን እንመለከታለን፡፡ ፡፡

የዐቢይ ጾም ሁለተኛው እሑድ ቅድስት ተብሎ ተሰይሟል። ቅድስት የሚለው ቃል ግሱ “ቀደሰ” ሲሆን “ለየ፣ አከበረ፣ መረጠ የሚል ትርጉም ሲኖረው፤- ቅድስት ማለት የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ማለት ነው። ቅዱስ የሚለው ቃል እንደ የአገባቡ ለፈጣሪም ለፍጡርም ያገለግላል። ለፈጣሪ ሲነገር እንደ ፈጣሪነቱ ትርጉሙ ይሰፋል፣ ይጠልቃል፡፡ ለፍጡር ሲነገር ደግሞ ቅድስናውን ያገኙት ከራሱ ከእግዚአብሔር ነው፡፡ “ያዘጋጃቸውን እነርሱን ጠራ፤ የጠራቸውንም እነርሱን አጸደቀ፤ የአጸደቃቸውንም እነርሱን አከበረ፡፡” እንዲል፡፡ (ሮሜ. ፰፥፴)

ዕለተ ሰንበት ቅድስት መባሏ በሰዎች እና በእግዚአብሔር መካከል ለቅድስና ሕይወት ምልክት ማስታወሻ እንድትሆን ነው። በባሕሪይው ቅዱስ የሆነ አምላክ ዓለምን የማዳን ሥራውን የጀመረበትን፣ ፅንሰቱን፣ እንዲሁም የማዳን ሥራውንም አጠናቆ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ዘለዓለማዊ ሕይወትን ያበሰረበትን ትንሣኤውን የምናስብበት በመሆኑ የዕለቱ ቅድስና፣ የፈጣሪን ቅዱስ ተግባር የምናደንቅበት፣ የዋለልንን ውለታ ከፍ ከፍ እያድረግን እርሱን የምናመሰግንበት ዕለት ነው። ይህም እኛን ወደ በለጠ የቅድስና ሕይወት የሚያሸጋግረን በመሆኑ የእግዚአብሔርን ጥልቅ ፍቅር በየጊዜው እንድናስብና በፍቅሩም እንድንኖር ያግዘናል፡፡

ዕለተ ሰንበት ነገረ እግዚአብሔር በተለየ ሁኔታ የሚዘከርባት ናትና “የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ” (ዘፀ. ፳፥፰) ተብሏል፡፡ የሰንበትን ቀን አስቀድሞ የቀደሰ፣ የባረከ ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ “እግዚአብሔርም ሰባተኛውን ቀን ባረከው፣ ቀደሰውም፤ እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ ዐርፎአልና“እንዲል፡፡ (ዘፍ. ፪፥፫)

“እንግዲህ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ” የተባለው እግዚአብሔር አስቀድሞ የባረከውን የቀደሰውን እኛ ድጋሚ የምንቀድስ የምንባርክ ሆነን ሳይሆን በዕለተ ሰንበት ራሳችንን በተለየ ሁኔታ ለቅዱስ ተግባር እንድንለይ፣ ለሥጋችን ከምንፈጽማቸው ተግባራት ይልቅ ለተግባረ ነፍስ እንድናደላ ያስረዳናል። ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት፤ ሐሤትን እናድርግ፥ በእርስዋም ደስ ይበለን።እንዳለው (መዝ. ፻፲፯፥፳፬)

በዕለተ ሰንበት የምእመናን መንፈሳዊ ሕይወት ይባረካል፣ ይቀደሳል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ “አንቀጸ ብፁዓን” በመባል የተጠቀሱትን መፈጸም ለክርስቲያን ሁሉ ይገባል፡፡ (ማቴ. ፭፥፩-፲፪) በዚህ ታሳቢነት ዕለቱም ዕለተ ቅድስና መሆኑን ለማጠየቅ ቅድስት ተብሏል። እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ (ዘሌ. ፲፱፥፪) ተብለናልና ቅድስት በተባለች ዕለተ ሰንበት ወደ ቤተ ክርስቲያን በመገስገስ ቅዳሴ በማስቀደስ፣ ቃለ እግዚአብሔር በመስማት፣ የታመመን፣ የታሠረን በመጠየቅ፣ በአጠቃላይ የቅድስና ሥራዎችን እንድንሠራ ለእኛ ለክርስቲያኖች ታዘናልና ተግባራዊ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ የቅድስና ሕይወት መሠረቱ የእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ መጠበቅና ማድረግ ሆኖ ሳለ ለመቀደስ የእኛ መሻት፣ መፈለግ ወሳኝ ነው።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጾመ ሰብአ ነነዌ

ጾመ ሰብአ ነነዌ፤ የነነዌ ሰዎች ጾም በነነዌ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ለሦስት ቀን የጾሙት ጾም ነው፡፡ የነነዌ ከተማ በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ የምትገኝ ስትሆን መሥራቿም ናምሩድ ነው (ዘፍ.፲፥፲፩-፲፪)፡፡ ጥንታዊቷ የነነዌ ከተማ ለአሦር መነሻ የሆነች፤ እጅግ ሰፊና ያማረች፤ የቅጥሯ ርዝመትም ፲፪ ኪሎ ሜትር የሚሸፈን ነበር፡፡ በከተማዋ ንጉሡ ሰናክሬም ብዙ ሕንጻዎችን ገንብቶ ነበር (ዮናስ ፬፥፲፩)፡፡

በዚያ ዘመን የነበሩ የነነዌ ሰዎች ኃጢአታቸው በዝቶ እግዚአብሔር ሊያጠፋቸው ሲል በዳግማዊ ኢዮርብዓም ዘመነ መንግሥት የነበረ ነቢዩ ዮናስን የስሙ ትርጓሜ ርግብ የሆነ ቸርነትና ምሕረቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር መክሮ፣ ዘክሮ እንዲመልሳቸውና ንስሓ እንዲገቡ ወደ ነነዌ ከተማ (ሕዝብ) ላከው (ሉቃ. ፲፩፥፴)፡፡ ይህ ነቢይ መኖሪያው በገሊላ በጋትሔፌር ድንበር ከተማ ነበረ፤ አባቱም አማቴ ይባላል፡፡ በዚያን ጊዜ ኢዮርብዓም ሶርያውያንን አባሮ የእስራኤልን ድንበር እንዲመልስ ነቢዩ ዮናስ ትንቢት ተናገረ (፪ኛነገ.፲፬፥፳፭፤ ዮናስ ፩፥፩)፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ያስነሣው የሰራጵታዋ መበለት ሕፃን ነቢዩ ዮናስ እንደ ሆነ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያስረዳል (፩ኛነገ.፲፯፥፲፱)፡፡

እግዚአብሔር አምላክም ሔደህ በነነዌ ላይ ስበክ ባለው ጊዜ ነቢዩ ዮናስ አንተ መሐሪ ነህ፤ ልትጠፉ ነው ብዬ ተናግሬ ብትምራቸው ሐሰተኛ ነቢይ እባላለሁ ብሎ የተባለውን ባለመታዘዝ እስራኤልን ለቆ በመርከብ ወደ ተርሴስ ሸሸ፡፡ እግዚአብሔርም ነቢዩ ዮናስ በመርከብ ሳለ ታላቅ ነፋስን አስነሥቶ መርከቧ በማዕበል እንድትመታ አደረገ፡፡ ዮናስ ግን በመርከቧ በታችኛው ክፍል እንቅልፉን ተኝቶ ያንኳርፍ ነበር፡፡ ከዮናስ ጋር በመርከቧ ተሳፍረው የነበሩ ነጋድያንም ያላቸውን ሀብት ወደ ባሕሩ መጣል ጀመሩ፡፡ የመርከቡም አለቃ ወደ ዮናስ ቀርቦ “ምነው ተኝተሃል? እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ያድነን ዘንድ ተነሥተህ አምላክህን ጥራ” አለው፡፡ (ዮናስ ፩፥፮) ተሳፋሪዎቹም ተጨንቀው ይህ ነገር ያገኘን በማን ምክንያት ነው?  ብለው ዕጣ ተጣጣሉ፤ ዕጣውም በነቢዩ ዮናስ ላይ ወደቀ፡፡

ነቢዩ ዮናስ ጥፋቱን ተገንዝቦ ማዕበሉ በእኔ ምክንያት የመጣ ስለሆነ ንብረታችሁን ሳይሆን እኔን ወደ ባሕር ጣሉኝ” በማለት ተማጸናቸው፡፡ እነርሱም ስለዚህ ሰው ነፍስ እንዳንጠፋ፣ ንጹሕም ደም በእኛ ላይ እንዳይደረግብን አይሆንም አሉ፡፡ ነገር ግን ዕጣ በተጣጣሉ ጊዜ ዕጣው በዮናስ ላይ ስለ ወጣ ነጋድያኑ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ ወዲያውኑ ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘ ታላቅ ዓሣ አንበሪ ዮናስን ዋጠው፤ እግዚአብሔርበበዓሣ አንበሪውም ሆድ ውስጥ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት አሳድሮ ወደ ነነዌ አድርሶ በየብስ ላይ ተፋው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የዮናስን ከዓሣ ሆድ መውጣት የራሱ ትንሣኤ ምሳሌ አድርጎ ነግሮናል (ማቴ.፲፪፥፲፱-፵፪፤ ሉቃ.፲፩፥፴-፴፪)፡፡

የእግዚአብሔርም ቃል ለሁለተኛ ጊዜ ወደ ዮናስ መጣ፡፡ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የነገርኩህንም የመጀመሪያውን ስብከት ስበክላት” አለው፡፡ ነቢዩ ዮናስም “በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለበጣለች” እያለ ሰበከ፡፡ (ዮናስ ፫፥፩)፡፡ የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ፤ ።ጾምም ዐዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፡፡ ወሬውም ወደ ነነዌ ንጉሥ ደረሰ፤ እርሱም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጎናጸፊያውን አወለቀ፤ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ፤ ሰዎችና እንስሳትም አንዳች እንዳይቀምሱ ውኃም እንዳይጠጡ ዐዋጅም አስነገረ፡፡ (ዮናስ ፫)

ዮናስ ግን ፈጽሞ አዘነ፣ ተከዘም፡፡ ምነው ቢሉ፡- ነቢዩ ዮናስ የእግዚአብሔር መሐሪነት፣ ቸርነቱም የበዛ እንደሆነ አውቋልና ቁጣውን በምሕረት እንደሚለውጥ ስለተረዳ “ሐሰተኛ ነቢይ እባላላሁ” በማለት ተበሳጨ፤ ከከተማይቱም ወጣ፡፡ ከፀሐዩ ግለት ይሸሸግ ዘንድ ጥጉን ያዘ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ቅሉን አዘዘለትና ከዮናስ ራስ ላይ ጥላ ትሆነው ዘንድ ከፍ ከፍ አደረጋት፡፡ ዮናስም ስለቅሊቱ ደስ አለው፡፡ ነገር ግን በነጋ ጊዜ እግዚአብሔር ትልቁን ትል አስነሥቶ ቅሊቱን መታ ቅሊቱም ወዲያው ደረቀች፡፡ ዮናስንም ፀሐዩ መታው፡፡ ተስፋ ቆርጦም “ከሕይወት ሞት ይሻለኛል” አለ፡፡

ቅጠሉ በመድረቁ ዮናስ ባዘነ ጊዜ እግዚአብሔር አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለሆኑ ያሳዝኑኛል” በማለት ነቢዩ ዮናስን ተናገረው፡፡ ውሸታም ላለመባል መኮብለሉም ስሕተት መሆኑን አስረድቶታል፡፡

ነቢዩ ዮናስ ሐሰተኛ እንዳይባልም ከሰማይ የወረደው እሳት እንደ ደመና ሆኖ ከላይ የታላላቅ ዛፎች ቅጠል እስኪጠወልጉ ድረስ አድርቆ ለሕዝቡ አሳይቷቸዋል፡፡ ንስሓቸው በከንቱ እንዳልቀረም አስረድቷቸዋል (ትንቢተ ዮናስ)፡፡ በሦስት ቀን ሱባኤም በንስሓ ተመልሰዋልና እግዚአብሔር ሊያመጣ ካለው መቅሰፍት አድኗቸዋል፡፡

ጾመ ነነዌ የእግዚአብሔርን ቸርነትና መሐሪነት የምናስታውስበት ጾም ነው፡፡ ይኸውም እኛ ፍጡራኑ በበደልን ጊዜ ፈጽሞ ከማጥፋት ይልቅ ምክንያት ፈልጎ እንድንድን ያደርገናል፡፡ ዮናስ ለስብከት ፈቃደኛ ባይሆን እንኳን እግዚአብሔር በተለየ ጥበቡ እንዲሔድ አድርጎታል፡፡ በእርግጥ እግዚአብሔር ሌላ የሚልከው ነቢይ አጥቶም አይደለም፤ እርሱንም ጭምር ሊያስተምረው ስለ ፈለገ እንጂ፡፡ የነነዌ ሰዎች የተነሳሕያን ምሳሌ ናቸው፡፡ ይህም ማለት ሰው ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ከገባ እግዚአብሔር ይቅር ማለቱን አይተውም፡፡ ለዚህም ነው ዮናስን ‹‹አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለ ሆኑ ያሳዝኑኛል›› ያለው፡፡

ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶቻችን ይህን እና ሌሎች አጽዋማትን እንድንጾም የወሰኑልን ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ሕጉ የተዘጋጀልን እንደ ነነዌ ሰዎች እኛም ጾመን፣ ጸልየን ከኃጢአታችን እንነጻ ዘንድ ነው፡፡ ዛሬ ዓለማችን በኃጢአት ማዕበል እየተናወጠች ባለችበት ወቅት እኛም እንደ ነነዌ ሰዎች ከበደላችን ብንመለስ እና ንስሐ ብንገባ ቸሩ ፈጣሪያችን እግዚአብሔር ይቅርታና ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ ስለ ሆነ ‹‹ወደ እኔ ተመለሱ፤ እኔም ይቅር እላችኋለሁ፤›› ይለናል፡፡

ስለሆነም በነቢዩ ዮናስ ላይ የተደረጉ ተአምራትንና ካለመታዘዝ የሚመጣ ቅጣት ቀላል አለመሆኑን በማስተዋል፣ ለነነዌ ሰዎች የወረደውን ምሕረት በመገንዘብ ለእግዚአብሔርም ሆነ ለሃይማኖት አባቶች እና ለወላጆቻችን መታዘዝ ይገባናል፡፡ ስንጾምም እግዚአብሔር አምላካችን መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት መልሶ በኃጢአት ለጠፋው ዓለም ይቅርታውን ይልካል፡፡ በመጾማችን ራሳችን ከመዓትና ከመቅሠፍት ከመዳናችን ባሻገር በእኛ በደል ምክንያት አገራችን፣ ዕፀዋቱና እንስሳቱም ሳይቀር ከድርቅና ከቸነፈር ይተርፋሉና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል” (ኤፌ ፪፥፳)

                                                                                  በኃይለ ኢየሱስ ዘጼዴንያ

                                                                                        ክፍል  -ሁለት 

      የሐዋርያት ጾም ስያሜና ቀኖናዊ መሠረቱ

ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር የመጣበትን መለኮታዊ ዓላማ አጠናቆ ወደ ባሕርይ አባቱ ከማረጉ በፊት ቅዱሳን ሐዋርያትን ሰብስቦ “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፤ ያዘዝኋቸውን ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” (ማቴ፳፰÷፲፱ -፳) በማለት ታላቁን ተልእኮ አዟቸው ነበር፡፡

በፍርሃት ውስጥ ሆነው ይህንን መለኮታዊ አደራ የተቀበሉት ሐዋርያት ለአገልግሎት ከመሰማራታቸው በፊት ከፍርሃታቸው የሚያላቅቃቸው፤ የሚያጽናናቸው እና የሚያበረታታቸው እንዲሁም ከሐሰተኛው ዓለም ለይቶ ወደ እውነት ሁሉ የሚመራቸው ሰማያዊ ኃይል ያስፈልጋቸው ነበርና “አንትሙሰ ንበሩ ሀገረ ኢየሩሳሌም እስከ ትለብሱ ኃይለ እም አርያም፤ እናንተ ግን ከአርያም ኃይልን እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ቆዩ፡፡”(ሉቃ ፳፬÷፵፱) የሚል ትእዛዝ ተነግሯቸው ተስፋም ተስጥቷቸው  ነበር፡፡
በተስፋውም መሠረት ኢየሩሳሌም በማርቆስ እናት በማርያም ቤት ሁሉም ተሰብስበው በጸሎት እየተጉና በአንድ ልብ ሆነው ይህንን ሕያው ተስፋ በመጠባበቅ ሳሉ ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን መካከል በተነሣ በኀምሳኛው ቀን  ባረገ በዐሥረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ እሳት ወረደላቸው፤ የፍርሃት መንፈስ ተወግዶ በምትኩ ደፋሮችና በብዙ ቋንቋዎች የሚናገሩ ሆኑ፤ በሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ስብከትም በአንድ ቀን ሶስት ሺህ  ነፍሳት አምነው ተጠመቁ፡፡

ዕለቱም የቤተ ክርስቲያን መመሥረት እውን የሆነበትና አዲስ ምዕራፍ የተከፈተበት ስለነበር የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን ተባለ፡፡ (የሐዋ. ፪÷፩-፵፯) የመንፈስ ቅዱስ ኃይል ተገልጦ ፍርሃትና ስጋታቸው የተወገደላቸው ቅዱሳን ሐዋርያት ለወንጌል አገልግሎት ከመሠማራታቸው በፊትና ሕገ ወንጌልን ከማስተማራቸው አስቀድሞ አገልግሎታቸው እንዲቃና፤ መንፈስ ቅዱስ እንዳይለያቸውና የመንፈስ ቅዱስን ምሪትና ኃይል ለመቀበል ሱባኤ ያዙ፡፡ ይህም ጾም “ጾመ ሐዋርያት” ወይም “የሰኔ ጾም” ተባለ፡፡ የሰኔ ጾም ለምን ተባለ ቢሉ ከክረምቱ መግባት ቀደም ብሎ ከወርኃ ሰኔ ጀምሮ የሚጾም በመሆኑ የሰኔ ጾም በሚል ስያሜ ይጠራል፡፡

ሐዋርያት የአገልግሎት መጀመሪያ የሆነውን ጾም ሲፈጽሙም ዓለምን በወንጌል ጨውነት ያጣፍጡ ዘንድ የሚያገለግሉበትን ክፍለ ዓለም ዕጣ በመጣጣል ዕጣው ወደ ደረሳቸው የአገልግሎት ቦታ መሰማራታቸውን የቤተ ክርስቲያን የታሪክ መዛግብትና ሊቃውንት አባቶቻችን ያስረዳሉ፡፡

ጾመ ሐዋርያት “የቀሳውስት ጾም” ወይስ የክርስቲያኖች ሁሉ ጾም?

የሐዋርያትን ጾም አንዳንዶች “የቀሳውስት ጾም ነው” ሲሉት ይሰማል፡፡ ይህም ከአሰያየሙ ጋር የተያያዘ ብዥታን በመጠቀም ላለመጾም የሚፈልጉ ወገኖች ያመጡት አስተሳሰብ ነው፡፡ እነዚህ ወገኖች “የሐዋርያት” የሚለውን ቃል ብቻ በመውሰድ ጥንት ይህንን ጾም ሐዋርያት ብቻ እንጂ ሕዝቡ አልጾመውም፤ ዛሬ ደግሞ በሐዋርያት እግር የተተኩ ካህናት (ቄሶች) ናቸውና ጾሙም የእነርሱ ነው ሲሉ ይደመጣሉ፡፡

ቤተክርስቲያን ግን ይህን የአዋጅ ጾም ጳጳስ፣ ቄስ/መነኩሴ፣ ዲያቆን፣ ሰንበት ተማሪ ምእመን ሳትል በ፵ እና በ፹ ቀን የተጠመቀና ዕድሜው ከሰባት ዓመት በላይ የሆነው ሁሉ እንዲጾም ዐውጃለች፡፡ እኛም እነርሱን ተከትለን፣ በእነርሱ ሥርዓት በመመራት፣ በሐዋርያት ላይ ያደረው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብት በእኛም ላይ እንዲያድርብን በየዓመቱ ጾመ ሐዋርያትን ሌሎችንም አጽዋማት አክብረን መጾም እንደሚገባን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል (ፍት.ነገ. ፲፭÷ ፭፰፮)፡፡

የሐዋርያት ጾም የሁላችንም ጾም ነው!!

            ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል” እንዳለ (ኤፌ ፪÷፳) በሐዋርያት መሠረትነት ላይ ለታነጽን ለእኛ ለክርስቲያኖች የሐዋርያት ጾም የእኛም ጾም ነው፡፡ ጾሙንም የምንጾመው የሐዋርያትን በረከት ለመሳተፍ፣ እነርሱ ድል ያደረጉትን ዓለም እንድናሸንፈው አምላካችንን ለመማጸን ነው፡፡ በዚህ ጾም ሐዋርያት ሁሉን ትተው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መከተላቸው፣ ዓለምን ዞረው ማስተማራቸውና ስለ ቅዱስ ስሙ በጽናትና በጥብዐት መከራ መቀበላቸው ይዘከራል፡፡ ምእመናን እና ካህናትም የቅዱሳን ሐዋርያትን መንፈሳዊ ተጋድሎ በማሰብ በዘመኑ ሁሉ በፍቅር በተዋበ መታዘዝ እንፈጽም ዘንድ ይገባል፡፡ (ፊልጵ. ፪÷፲፪) ከልብ ንስሓ በመግባት፣ ከምጽዋትና ከጸሎት ጋር፣ እግዚአብሔር ደስ በሚሰኝበት መንገድ ከግብዝነት ሕይወት በጸዳ መልኩ እንጹም፡፡ ከጸሎትና ከምጽዋት ጋር በሚገባ ጾመን ከራሳችንን እና ከእግዚአብሔር አምላካችን ጋር የምንታረቅበት ሱባኤ ያደርግልን ዘንድ፤ የቅዱሳን አባቶቻችን ሐዋርያት በረከትና ጸሎት አይለየን፡፡