ጾመ ሐዋርያት

አባ ዐሥራት ደስታ

    ጾም ከክርስቲያናዊ ምግባራት ውስጥ አንዱ ነው፡፡ ጾም አንድን ክርስቲያን ክርስቲያን ከሚያሰኙት ሥራዎች እና በእግዚአብሔር ዘንድም እንዲወደድ ከሚያደርጉን ተግባራት ውስጥ አንዱ ነው፡፡ ክርሰቲያን ማለት የክርሰቶስ ወገን፤ አካል፤ ቤተሰብ፤ ደቀ መዝሙር ማለት ነው፡፡ ክርስቲያን ክርሰቶስን መስሎ የሚኖር ሰው ነው፡፡ ይህ ደግሞ ሕይወትን በጾም በጸሎት በመምራት ራስንም ከክፋት በመጠበቅ መልካም ሥራንም በመሥራት ራስን በቅድስና በመጠበቅ የሚገልጥ ተግባር ነው፡፡ እኔ ክርስቲያን ነኝ እያለ ግን  ‹‹ይህ ጾም የቄሶች ነው፤ የሰኔ ጾም ነው›› እያለ ምክንያትን የሚያቀርብ ‹‹ክርስቲያን›› እርሱ ራሱን መፈተሸ መመርመር ይገባዋል፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያን ተግባሩ ሐዋርያትን የሚመስል መንፈሳዊ ሰው ነውና ፡፡

 ጾም ራስን ለእግዚአብሔር ለማስገዛት ከኃጢአትም ለመራቅ ራስን ፍላጎትን ሃሳብን ችግር እና ምኞትንም ለእግዚአብሔር ለመግለጽ እርሱ ከክፋት እዲጠብቀን ለማድረግ ራስን ቤተሰብን አሳልፎ ለእርሱ መስጠት ነው ፡፡ በሃሳብ በተግባር እና በምኞትም ቅዱሳንን የመምሰል የመሆን ተግባር ነው ፡፡ ጾም መታቀብ መለየት ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ስለ ሠራነው ክፉ ሥራ ኃጢአት እና በደል ማዘን ማልቀስ ማንባት ለምሕረት ለቸርነት እና ለይቅርታ የእግዚአብሔርን ደጅ መጥናት ነው ፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓተ እምነት መሠረት ጾም የአዋጅ እና የግል ጾም ተብሎ በሁለት ይከፈላል፡፡ የአዋጅ ጾም የሚባለው ሁሉም ክርሰቲያን በታወቀ እና በተረዳ መንገድ የሚፈጽሙት ጾም በአንድ ሐሳብ እና በአንድ ልብ የሚጾሙት ሲሆን እነርሱም ፡-

  1. ጾመ ነቢያት፤
  2. ጾመ ነነዌ፤
  3. ዐቢይ ጾም፤
  4. ጾመ ሐዋርያት፤
  5. ጾመ ድኅነት (የረቡዕ እና የአርብ ጾም)፤
  6. ጾመ ፍልሰታ፤ እና
  7. ጾመ ገሀድ ናቸው፡፡

ሌላው የጾም  አይነት ደግሞ የግል ጾም ነው፡፡ የግል ጾምን የፈቃድ ወይንም የንሰሐ ጾም ማለት እንችላለን፡፡ ይህ ስለደበላችን ስለ ጥፋታችን እና ስለ ሠራነው ክፉ ኃጢአት እግዚአብሔር ምሕረት ቸርነት እና ይቅርታውን እንዲሰጠን ብለን ከንሰሐ አባታችን ጋርም በመነጋገር የምንፈጽመው ጾም ነው ፡፡

 ጾመ ሐዋርያት የሚባለው ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ የሆነውና ከጰራቅሊጦስ (ርደተ መንፈስ ቅዱስ) ቀጥሎ እስከ ሐምሌ አምስት ቀን ድረስ የሚጾም ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም በአላዋቂዎች ወይም የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና ትውፊት ባልተማሩ ዘንድ ‹‹የቄስ ጾም›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ይህ አባባል ራስን በሰዎችና በእግዚብሔር ዘንድ ያሳንሳል እንጂ አያስከብርም፡፡ ይህን ጾም ማንኛውም ክርስቲያን የሆነ ሰው ሁሉ መጾም ያለበት ክርስቲያናዊ ተግባር እና ግዴታም ጭምር ነው፡፡

  ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ለስብከተ ወንጌል ወደ መላው  ዓለም ከመሠማራታቸው በፊት  በአንድነት፣ በሰላምና  በፍቅር  የጾሙት ጾም ነው፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ ጾመ ሐዋርያት በድሜጥሮስ የበዓላት አቆጣጠር ስሌት (መባጀ ሐመር) ከፍና ዝቅ ስለሚል  የተወሰነ ቀን የለውም ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከአርባ ቀን ይበልጣል አንዳንድ ጊዜም ከሠላሳም ያንሳል፡፡ ለምሳሌም፡- በ2010 ዓ.ም ግንቦት 20 ተጀምሮ 43 ቀን ተጹሟል፡፡ በ2011 ዓ.ም ደግሞ ሰኔ 10 ይጀመርና ለ25 ቀን ይጾማል ማለት ነው፡፡

   ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ፍርሃት፣ ጭንቀት፣ ሥጋት ቀርቶላቸው በመላ ሰውነታቸው የተረጋጋ ሕይወትና ሰላም ነግሦባቸዋል ፡፡ ምንም እንኳን ክርስቶስን በመስበካቸው ከአረማውያንና ከአላውያን መከራ ቢበዛባቸውም የልብ ደስታ ይሰማቸው ነበር፡፡  በምግባር ፣በሃይማኖት  ጸንተው በነገሥታት ፊት ያለዕረፍት  በድፍረት ቃለ እግዚአብሔርን እያስተማሩና ግፈኞችን እየገሰጹ በጥብአት ለሰማዕትነትለ ደርሰዋል ጌታችንም በዚሁ ሥራቸው አክብረዋል፡፡

   ሐዋርያት ከብልየት የተለዩት በአእምሮ የጎለመሱት ከፍጹምነት የደረሱት መንፈሰ ቅዱስን በመቀበላቸው ነው፡፡ በዘመነ ብሉይ እንደ ቤት አድሮባቸው አካላቸውን እንደ ልብስ  ልቦናቸውን እንደ መቅደስ አድርጎ ነቢያትን ትንቢት ያናገረ የእግዚአብሔር ቅዱስ መንፈስ ከሐዋርትም ሕጸጽ (ጥርጥርን) አጥፍቶላቸው ለቅድስናም አብቅቶአቸዋል፡፡

    ወላጆች ለልጆቻቸው መልካምና ደስ የሚያሰኝ ስጦታን መስጠት እንዲፈቅዱ ሁሉ እግዚአበሔርም ለቅዱሳን ሐዋርት ከቅዱስ መንፈሱ በመሰጠቱ እነርሱም የዲያብሎስን ውጊያ የማቸነፍ ችሎታንና በርኩሳን መናፍስት ላይ ኃይልን የመገሰጽ ሥልጣን በጾምና በጸሎት ተላብሰዋል፡፡

   ስለዚህ እኛም በክርስቶስ ክርስቲያን በወልድ ውሉደ እግዚአብሔር የተባልን የእግዚአብሔር የጸጋ ልጆች የእግዚአብሔርን ሕልውና ከመንፈስ ቅዱስ ከተረዳንና ካወቅን በኋላ በሥጋ ሥራ ተገፋፍተን  ሃይማኖታችን ብንክድ አምላክን ሥራ ብንነቅፍ የመመለስና በሕይወት የመኖርም ተስፋ የለንምና በትሁት ስብእና በንቁ ኅሊና ራሳችንን ለሕገ እግዚአብሔር በማስገዛት የጾምና ጸሎት ወዳዶች እንሁን እንደ ሐዋርያት በክርስቶስ ዘንድ አሸናፊዎች እንሆናለንና፡፡ ጾሙን ጹመን የነፍስ ዋጋን እንድናገኝበት የእርሱ መልካም ፈቃድ ይሁንልን አሜን ፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *