ግቢ ጉባኤያት በቤተ ክርስቲያን

ቅዱስ ያሬድ “ሀገረ ክርስቶስ አዳም ወሠናይት ከመ ፀሐይ ብርህት ወከመ መርዓት ሥርጉት፤ የክርስቶስ ሀገር በጣም ያማረች፣ እንደ ፀሐይ የበራች እንደ ሙሽራም የተሸለመች ናት” በማለት የሚገልጻት ቤተ ክርስቲያን እናት ልጇ ምግብ አልበላላት ሲል ከምትጨነቀው ጭንቀት የበለጠ እናት ቤተ ክርስቲያን ከደገሰችው ድግሥ ልጆቿ አልመገብ ሲሉ ዘወትር ታዝናለች ትተክዛለች።(ጾመ ድጓ ዘምኵራብ)

የደገሠችልን ድግሥም ዛሬ በልተነው ነገም የሚያሻን አብዝተን ብንበላው ሕመም የሚያመጣብን ሳይሆን ከማርና ከስኳር ይልቅ ለሕይወታችን አስፈላጊ የሆነውን የእግዚአብሔር ቃል፣ ሕይወት የሚሆነን ሥጋ ወ-ደሙን ነው።

ነገር ግን የመጀመሪያው ሰው አዳም “በገነት ካለው ዛፍ ሁሉ ብላ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያሳየውና ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትምታለህና፡፡” ተብሎ የተነገረውን ትእዛዘ እግዚአብሔር በመተላለፍ በልቶ የሞት ሞትን እንደሞተ ሁሉ ዛሬ ደግሞ ሥጋዬን ብሉ ደሜን ጠጡ በሕይወትም ትኖራላችሁ ቢለንም ባለመብላት ወደ ሞት መንገድ ጉዞ የጀመርን ብዙዎች ነን። ((ዘፍ. ፪፥፲፮-፲፯)

መድኃኒት የሚያሻው ለታመመ እንደሆነ ሁሉ በኃጢአት የታመመ ብዙ ነው፡፡ በተለይም ወጣቱ ትውልድ ግንባር ቀደሙን ቦታ ይይዛል። ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚገቡ ተማሪዎች ከተለያዩ አካባቢዎች እንደመሰባሰባቸው የተለያየ የሕይወት ተሞክሮ ያላቸው በመሆኑ ልጓም የሚሆናቸው መንፈሳዊ ዕውቀት ካላገኙ በተለያዩ የኃጢአት ደዌያት እንደሚያዙ የሚያጠራጥር አይደለም።

ከቤተሰብ፣ ከዘመድ ርቀው በመኖራቸው ነፃነት ስለሚያገኙ ከመንፈሳዊው ሕይወት ይልቅ መጥፎ በሆነ ሱስ ራሳቸውን የሚደብቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ በሥጋዊ ሥራዎች (በዝሙት፣ በምንፍቅና፣ በዘረኝነት) በሽታ ተይዘው ክርስቲያናዊ ሕይወታቸውን፣ ኢትዮጵያዊ ማንነታቸውን ያጣሉ። ይህን ፈተና እንዲቋቋሙ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን በተደራጀ መንገድ እንድትቀጥል ግቢ ጉባኤ ሰፊውን ድርሻ ይይዛል።

ግቢ ጉባኤያት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓቷና ትውፊቷን ይዛ ከማስቀጠል አንጻር ምን ሠራ?

ቤተ ክርስቲያን ማለት እያንዳንዱ ምእመን፣ ሕንጻው፣ ኅብረታችንን ማለታችን እንደሆነ ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታየ “ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን” በሚለው መጽሐፋቸው ገልጸውታል። የመጀመሪያው እያንዳንዱ ክርስቲያን ትውልድ እንዲቀጥል የድርሻውን እንዲወጣ ማድረግ ነው። እያንዳንዱ ክርስቲያን እንዲቀጥል ማድረግ  ማለት  አባት  እናት  ሲሞት ልጅ  ይተካል። ተተኪው ትውልድ ከሚባለው ውስጥ ደግሞ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚያልፉት  ይገኙበታል። ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም አስተምህሮዋን ዶግማዋን ቀኖናዋን እና ትውፊቷን ይዛ የምትቀጥለው ርትዕት የሆነችውን  የአባት  የእናቱን  ሃይማኖት  ጠንቅቆ  ባወቀ  ትውልድ  ነው።  ለዚህ ደግሞ  ግቢ  ጉባኤያት  አስፈላጊ  ናቸው።

ሁለተኛው የክርስቲያኖች ኅብረት ነው። እያንዳንዱ ክርስቲያን ትውልዱን ማስቀጠል ከቻለ የክርስቲያኖች ኅብረትም ይቀጥላል፡፡ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሰባሰቡ ተማሪዎች ከሀገራችን ከሁሉም  አቅጣጫ የሚመጡ  ስለሆነ  ግቢ ጉባኤያት  ላይ  በሚገናኙበት  ወቅት የአኗኗር ባህላቸው ሳያግዳቸው እርስ  በእርሳቸው  ተግባብተው አንዱ ከሌላው እየተማረ በሃይማኖት፣ በምግባር በጎ  ነገር  የሚማሩበት ነው። ስለዚህ ሰው ከጎረቤቱ ጋር መኖር በከበደው በዚህ ዘመን ኢትዮጵያዊ አንድነት ብለን የምናቀነቅነውን ሐሳብ እየታደጉ ያሉት እነዚህ  የግቢጉባኤያት ተማሪዎች ናቸው።

በክርስቲያናዊ መዋደድ የሚዋደዱ፣ የሚረዳዱ፣ የሚተሳሰቡ ተማሪዎችን ብንፈልግ ከፍ ያለውን ቦታ የሚይዙት የግቢ ጉባኤያት ፍሬዎች ናቸው። ለማኅበራዊ አንድነትም ከፍ ያለ አስተዋጽኦ እንዳለው በዚህ መረዳት ይቻላል። የክርስቲያኖች ኅብረት እንዲታነጽ፣ እንዲቀጥል ያደርጋልና።

ሦስተኛው፡- ክርስቲያኖች እስካሉ ድረስ ሥርዓተ አምልኮን ለመፈጸም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን መኖር አለበት። ቤተ ክርስቲያን የምትታነጸውም በሃይማኖቱ በጸና፤ አስተምህሮዋን ተረድቶ ለአገልግሎት ራሱን ባዘጋጀና ለሌሎች ፍቅር በሚሰጥ፣ ዛሬን ብቻ ሳይሆን ወደፊትን አሻግሮ ማየት በሚችል ትውልድ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ግቢ ጉባኤያት ከፍ ያለ አበርክቶት አላቸው።

ዛሬ ላይ በግቢ ጉባኤያት ያለፉ ልጆች አንዳንዶቹ አራቱ ባሕርያተ ሥጋ ተስማምተውላቸው ዓለምን ንቀው መንነው ለሀገር ሰላም እና አንድነት ይለምናሉ፤ አንዳንዶቹ በሥርዓተ  ቤተ ክርስቲያን ጸንተው  በዲቁና፣ በሕግ እየኖሩ ማለትም (በቅስና) እያገለገሉ ይገኛሉ። አንዳንዶች የዘመናዊ ትምህርታቸውን እንደጨረሱ ጉባኤ ቤት ገብተው የሚማሩም አሉ። የተማሩት ደግሞ እንደ አባቶቻቸው ወንበር ተክለው የሚያስተምህሩም አሉ።

በሃይማኖት ዐይን ለተመለከተው ይህ ቀላል የሚባል አይደለም። “ግንቦት ልደታን ለግቢ ጉባኤ” በማለት ሳምንቱ የግቢ ጉባኤ ሳምንት እንዲሆን የተደረገውም እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ ወደፊት ግቢ ጉባኤ ከዚህ የተሻለ አሠራር እንዲኖረው ለቤተ ክርስቲያን፣ ለሀገር የሚጠቅም ትውልድ ለመፍጠር በማሰብ ነው።

የአንድ ሳምንት የገንዘብ ማሰባሰብ ዓላማውም ቅዱስ ጳውሎስ “ስለዚህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉምና።”  (፪ኛጴጥ. ፩፥፲) እንዲል በአእምሮ የጎለመሱ፣ በጥበብ ያደጉ፣ ዘመኑን የዋጁ የቤተ ክርስቲያንን ልጆች የበለጠ ማትጋት ስለሚያስፈልግ ግቢ ጉባኤያትን ማጠናከር ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር በመሆኑ የግቢ ጉባኤ ባለአደራዎች የተጣለባችሁን ኃላፊነት እና አደራችሁን ተወጡ።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *