የቅድስና ሕይወት

ለሜሳ ጉተታ

ቅድስና የሚለው ቃል ቀደሰ ፤ አከበረ ፤ አነጻ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ነው ፡፡ የቅድስና ባለቤት ምንጭ እና መሠረት እግዚአብሔር ሲኾን ቅድስናውም የባሕርይ ገንዘቡ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሌሎች ማለትም ሰዎች፣ ቀናት፣ ንዋያት፣ ቦታዎች፣ ምስጋናና የመሳሰሉት ለእግዚአብሔር ሆነው ሲለዩና ሲቀርቡ ቅዱስ ይሆናሉ፡፡ ይህ የተሰጣቸው ቅድስና የእግዚአብሔር ከመሆናቸው የተነሣ የሚያገኙት በመሆኑ የጸጋ ቅድስና ይባላል፡፡ የእግዚአብሔር ቅድስና ግን የባሕርይ ገንዘቡ ነው ፡፡

ከላይ የሠፈሩትን ሀሳቦች መሠረታዊ መልእክት ስንመለከት የቅድስና ሕይወት ባለቤት እግዚአብሔር መሆኑንና ሰዎችም ይቀደሱ ዘንድ ፈቃዱ መሆኑን እንረዳለን፡፡ ለቈላስይስ ምእመናን የተላከው የቅዱስ ጳውሎስ መልእክትም ከተገለጸው መልእክት በተጨማሪ ሰውን ወደ ቅድስና የሚያደርሱ የተጋድሎ መስመሮችን ያሳያል፡፡ እነዚህ ምሕረትና ርኅራኄ፣ ቸርነትና ትሕትና፣ የዋህነት፣ ትዕግሥት፣ ይቅር መባባልና ፍቅር፣ ማመስገንና ቅዱስ ቃሉን መማር፣ ራስን ማስተማርና መገሠጽ ወደ ቅድስና ሰገነት የሚያወጡ/የሚያደርሱ መሆናቸውን ከጥቅሱ እንገነዘባለን ቈላ. 3፥12-18.

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንደኛ ወጣቶች ሁነው ኃጢአትን አሸንፈው የኖሩ ለቅድስና ማዕርግም የበቁ ብዙ ወጣቶችን በምሳሌነት ማንሳት ይቻላል፡፡ በእነዚህ ቅዱሳን ዘመን የእምነት እና የሃይማኖት ነጻነት የለም፡፡ እግዚአብሔርን ማምለክ ማመስገን ለእርሱ መገዛት አይቻልም፡፡ በሕግ የተከለከለ እና የተገደበ እርሱን አምልኮ አመስግኖ ለእርሱ ተንበርክኮ የተገኘ ሁሉ ይቀጣ ነበር፤ ይታሰራል፤ ይገረፋል፤ ለእሳትና ለአንበሶች እራትም ይሆናል፡፡ እነርሱ ግን ለእርሱ ካላቸው ፍቅርና ቅንነት በእምነታቸው ጽናት ለጣዖት አልሰገዱም፣ አላመለኩምም፡፡ ይህንን ሁሉ ግን የፈጸሙት በእምነትና በተጋድሎ ነው ፡፡

ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ብሎ ገልጾታል፡- “እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ ስለ ሶምሶንም ስለ ዮፍታሔም ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና። እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፤ ጽድቅን አደረጉ፤ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ። ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ። እነዚህም ሁሉ በእምነታቸው ተመስክሮላቸው ሳሉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አላገኙም፥ ያለ እኛ ፍጹማን እንዳይሆኑ እግዚአብሔር ስለ እኛ አንዳች የሚበልጥ ነገርን አስቀድሞ አይቶ ነበርና” (ዕብ.11፡23-40)።

ዛሬ እኛ በአንጻራዊነት ሲታይ የእምነትና የሃይማኖት ነጻነት አለን፡፡ ያለ እኛ ፈቃድ ከእግዚአብሔር ሌላ እንድናመልክ የሚያስገድድ አካል የለም፤ ሰሞኑን በሀገራችን እየታዩ ያሉ የአህዛብ ጥቃቶችና የሰማእታቱ ጥብዐት እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡ ከዚህም በላይ ግን በራሳችን ፍላጎት እና ምኞት ተስበን ከእርሱ ልጅነት እንዳንወጣ፣ ከዘላለማዊ ሕይወትም እንዳይለየን ጥንቃቄ ልናደርግ ይገባል፡፡ እንጸና ዘንድም እነ ዳንኤልን እና ሠለስቱ ደቂቅን እንደ መልካም አርዓያ ማንሳት ይቻላል፡፡ እምነት ሥራን ይፈልጋል፡፡ ይህም ሲባል ማመን አንድ ጉዳይ ሲሆን እምነትን ወደ ተግባር መለወጥን፣ የምግባር ሰው መሆንን፣ ተጋድሎና ክርስቲያናዊ ግዴታዎችንም መፈጸምን ይፈልጋል፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *