ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር

ክፍል ሦስት

በእንዳለ ደምስስ

“ትምህርቴን በስኬት እንዳጠናቅቅ የረዳኝ ግቢ ጉባኤ ነው” (ዲ/ን አሰፋ አያሌው)

የክፍል ሦስት እንግዳችን ምሥራቀ ግዮን ኮሌጅ (የግል ኮሌጅ) በነርሲንግ ትምህርት ክፍል ተመራቂ የሆነው ዲ/ን አሰፋ አያሌው ነው፡፡ ዲ/ን አሰፋ ደሴ ከተማ ውስጥ ከሚገኘው ምሥራቀ ግዮን ኮሌጅ (የግል ኮሌጅ) በነርሲንግ ትምህርት ክፍል ከኮሌጁ ሦስት ነጥብ ዘጠኝ ሰባት (3.97) በማምጣትና ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ለመሆን በቅቷል፡፡

ዲ/ን አሰፋ የምሥራቀ ግዮን ጉባኤ ተሳታፊ የነበረ ሲሆን ከትምህርቱ በተጨማሪ የአብነት ትምህርቱን ተከታትሎ ዲቁና ተቀብሏል፤ ዐራተኛ ዓመት ላይ ደግሞ የተመራቂዎች ኮሚቴ (Graduation Committee) ሰብሳቢ ሆኖም አገልግሏል፡፡

ኮሌጅ ከገባ በኋላ የገጠመውን ሲገልጽ፡- “ኮሌጅ እንደገባሁ ግቢ ጉባኤ ውስጥ ለመሳተፍ አልሞከርኩም፡፡ ነገር ግን ከሁለተኛ ዓመት ጀምሮ ያለማቋረጥ ነው በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠውን ተከታታይ ትምህርት ለመማር የቻልኩት፡፡ ጊዜዬን በእቅድ እንድጠቀምና ከመደበኛ ትምህርቴ ጋር አጣጥሜ እንድጓዝ፣ በስኬታማነት እንዳጠናቅቅም የረዳኝ ግቢ ጉባኤ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ግቢ ጉባኤ ውስጥ መሳተፍ እንደጀመርኩ የአብነት ትምህርቱንም ጎን ለጎን መከታተል ጀመርኩ፡፡ በዚህም መሠረት የእግዚአብሔር ፈቃድ ሆኖ ተሳክቶልኝ ዲቁና ለመቀበል በቅቻለሁ፡፡ አሁንም ከግቢ ከወጣሁ በኋላ የአብነት ትምህርትን ለመማር እንደ እቅድ ይዣለሁ፡፡ “ በማለት ግቢ ጉባኤ በሕይወቱ ውስጥ ያሳረፈውን በጎ ተጽእኖ ይገልጻል፡፡

የጊዜ አጠቃቀምን በተመለከተም፡- “የመጀመሪያ ዓመት ላይ ጊዜዬን በአግባቡ ለመጠቀም አልሞከርኩም በተቃራኒው ሌሎች ጓደኞቼን ለመምሰልና በዙሪያዬም የነበሩ ሊያዘናጉ ከሚችሉ ነገሮች ለመራቅ እንኳን ሙከራ አላደርግም ነበር፡፡ ነገር ግን ግቢ ጉባኤ መሳተፍ ከጀመርኩ በኋላ በጊዜ አጠቃቀም ዙሪያ ምክርና ትምህርትም ይሰጠን ስለነበር በትክክል ተጠቅሜበታለሁ፡፡ ዐራተኛ ዓመት ላይ ግን የተመራቂ ተማሪዎች ኮሚቴ ሰብሳቢ (Graduation Committee) ሆኜ ማስተባበር ተጨምሮብኝ ስለነበር ትንሽ ሁሉንም አጣጥሞ ለመጓዝ ከብዶኝ ነበር፡፡ መደበኛ ትምህርቴ፣ ግቢ ጉባኤ፣ የአብነት ትምህርቴ፣ ጥናት እና የተመራቂ ተማሪዎች ኮሚቴ ሰብሳቢ መሆኑ አጨናንቆኝ የነበረ ቢሆንም እግዚአብሔር ረድቶኝ ከዩኒቨርሲቲው ሦስት ነጥብ ዘጠኝ ሰባት አጠቃላይ ውጤት በማምጣት የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ለመሆን በቅቻለሁ፡፡ ግቢ ጉባኤ በመንፈሳዊ ሕይወቴ ጠንክሬ መጓዝ እንድችልና ውቴታማ ሆኜ ከግቢው እንደወጣ አስችሎኛል”ሲል ተሞክሮውን ገልጾልናል፡፡

ዲ/ን አሰፋ ያጋጠሙትን ችግሮች በተመለከተ ሲገልጽም “ዐራተኛ ዓመት ላይ የመመረቂያ ዓመት ስለነበር የጊዜ እጥረት እየገጠመኝ እየተጨናነቅሁ በአግባቡ መጓዝ አቅቶኝ ነበር፡፡ በተለይም ከምረቃ ጋር ተያይዞ በርካታ ሥራዎችን እንሠራ ስለነበር በከፍተኛ ሁኔታ የጥናት ጊዜዬን ይሻማብኝ ነበር፡፡ በተጨማሪም ከዩኒቨርሲቲው መውጫ ፈተና (Exit Exam) ዝግጅት ጋር ተያይዞ ማጥናትን ይጠይቅ ስለነበር ከባድ ጊዜ ለማሳለፍ ተገድጄ ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር አግዞኛልና ጎዶሎነቴን እየሞላ በጥሩ ውጤት ለማጠናቀቅ ችያለሁ፡፡”

ዲ/ን አሰፋ እርሱ ያለፈበትን ሕይወት መነሻ በማድረግ ባስተላለፈው መልእክትም “ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚገቡ ተማሪዎች የምመክረው ከመጀመሪያው ጀምሮ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ለመሳተፍ ወስነው መምጣትና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ነው፡፡ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ማሳለፋቸው ጠንካሮችና የዓላማ ሰው እንዲሆኑ ያስችላቸዋል፡፡ እኔ በመጀመሪያ ዓመት ላይ በግቢ ጉባኤ አለመሳተፌ ውጤቴ ላይ ዋጋ አስከፍሎኛል፡፡” ሲል መልእክቱን አስተላልፏል፡፡

ልዩ ማስታወሻ ከአዘጋጁ፡-

ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ አንስቶ ላለፉት ሠላሳ አንድ ዓመታት ግቢ ጉባኤ ላይ በመሥራት የተጣለበትን አደራና ኃላፊነት ለመወጣት ክፍተኛ ጥረት አድርጓል፣ በማድረግም ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም ጥረቱ በርካቶችን በየከተኛ ትምህርት ተቋማት መሠረታዊ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በማስተማር በአባቶች ቡራኬና በአደራ መስቀል እያስመረቀ ይገኛል፡፡ ብዙዎችም ለውጤታማነታቸው ማኅበሩ በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠውን መንፈሳዊ ትምህርት በመከታተላቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲያውቁ፣ እምነታቸውን ጠንክረው እንዲይዙ፣ በሥነ ምግባር ታንጸው በየተሠማሩበት ቦታና ሙያ ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን በማገልግል የድርሻቸውን መወጣት እንዲችሉ እንደረዳቸው ይመሠክራሉ፡፡

የተከበራችሁ የድረ ገጻችን ታዳሚዎች በተከታታይ በሦስት ክፍል የወንድሞችና የእኅቶች ይግቢ ጉባኤ ተሞክሮ ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ነውና ወደፊት የሚገቡ ተማሪዎች አርአያነታቸውን ተከትለው እንዲጓዙ ያደርጋቸዋል በሚል ከብዙ በጥቂቱ ያቀረብንበትን ዝግጅት በዚሁ እንቋጫለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *