መጻሕፍት ክርስቶስ ሰው እንደሆነ እንደሚነግሩን አምላክ እንደሆነም ይነግሩናል

 

  • የማይመረመር፣ የማይለወጥ ቃል ሥጋን ተዋሐደ፤ መለወጥ ይስማማው የነበረ ሥጋን የማይለወጥ አደረገው፡፡ ስለዚህም በተዋሐደው በመዋቲ አዳም ሥጋ ተገለጠ፡፡ (እልመስጦአግያ)
  • ከእመቤታችን ከቅድስት ደንግል ማርያም የተወለደው የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ነው፤ እርሱም የባሕርይ አምላክ ነው፤ መለኮት ቢያድርበት በጸጋ የከበረ አይደለም፡፡ ሥጋን በመንሣት ሰው የሆነ እርሱ ብቻ ነው፤ በመለኮት የእግዚአብሔር ልጅ ነው፣ አምላክ ነው፡፡ ወልድ አንድ ብቻ ነው፡፡ (ቅዱስ አትናቴዎስ)
  • በሰው ባሕርይ ሰው የሆነ እርሱ ነው፤ ከአብ የተወለደ፣ ከባሕር አምላክ የተገኘ የባሕርይ አምላክ የዘለዓለም ንጉሥ እርሱ ነው፡፡ (ሐዋርያት)
  • ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል በእመቤታችን በንጽሕት ድንግል ማርያም ማኅፀን አደረ፤ ስለ መለኮት ተዋሕዶ በዚህ በምንናገርም በወልድ ያለውን ነው፡፡ ስለ አብ ስለ መንፈስ ቅዱስ ሰው ለመሆን በድንግል ማኅፀን አደሩ አንልም፡፡ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ወልድ ብቻ ከእርሷ ተወለደ እንላለን፡፡ (ቅዱስ አግናጥዮስ)
  • በቤተልሔም ተወለደ፣ በጨርቅ ተጠቀለለ፣ በበረት ተጣለ፤ ከብት ጠባቆች አዩት፣ መላእክት አመሰገኑት፣ ሰብአ ሰገል ሰገዱለት፡፡ (ቅዱስ ሄሬኔዎስ)
  • ከእመቤታችን ከንጽሕት ድንግል ማርያም ሥጋችንን ነሥቶ የተዋሐደው እርሱ ነው፤ ሥጋ ከመሆን በቀር ያለ መለየት ያለ መለወጥ ከአብ ጋር አንድ ነው፤ በሥጋም ያለመለይት ከእኛ ጋር አንድ ነው፡፡ (ቅዱስ ጎርጎርዮስ)
  • ከአብ የተወለደ፣ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሚሆን የእግዚአብሔር ቃል ሰው ሆነ፤ በመለኮቱ መዋረድ ሳይኖርበት በፈቃዱ ተዋርዶ የተገዥ ባሕርይን ተዋሐደ፡፡ ሰው ሆይ ሥጋ ያልነበረው እርሱ ለአንተ ብሎ ሥጋን ተዋሐደ፤ ሰው ሆይ በመለኮቱ የማይዳሠሥ የነበረ ነፍስና ሥጋን የተዋሐደ ቃል ለአንተ ብሎ ተዳሠሠ፤ በመለኮቱ ጥንት የሌለው እርሱ ጥንት ያለውን ፍጹም ሥጋን ተዋሐደ፡፡ (ቅዱስ አጢፎስ)
  • የከበሩ መጻሕፍት ክርስቶስ ሰው እንደሆነ እንደሚነግሩን አምላክም እንደሆነ እነርሱ እንዲሁ ይነግሩናል፡፡ ግዙፍ እንደሆነ እንደሚነግሩን ረቂቅም እንደሆነ፡፡ የእግዚአብሔር ቃልም እንደሆነ እርሱ ራሱም እግዚአብሔር እንደሆነ እንዲሁ ይነግሩናል፡፡ ከንጽሕት ድንግል ማርያም በኋላ ዘመን እንደተወለደ እንደሚነግሩን ቀድሞም ከአብ እንደተወለደ እንዲሁ ከአባት ያለ እናት፣ ከእናት ያለ አባት ለመወለድ መዠመሪያ እርሱ እንደሆነ ይነግሩናል፡፡ (ሄሬኔዎስ)
  • ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከሕይወት የተገኘ ሕይወት ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው ልጁን ወደዚህ ዓለም ላከው፤ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የእኛን ባሕርይ ይዋሐድ ዘንድ ጌትነቱንም ወደ ማወቅ ያደርሰን ዘንድ ነው፡፡ (ቅዱስ ጎርጎርዮስ)
  • እግዚአብሔር ቃል ወደዚህ ዓለም ይመጣ ዘንድ ከንጽሕት ድንግል ማርያም ሥጋን ይዋሐድ ዘንድ ምን አተጋው? በጨርቅ ይጠቀለል፣ በበረት ይጣል ዘንድ ከሴት(ከድንግል) ጡት ወተትን ይጠባ ዘንድ በዮርዳኖስ ይጠመቅ ዘንድ ምን አተጋው? (ቅዱስ እለእስክንድሮስ)
  • ለመወለዱ ጥንት በሌለው አስቀድሞ ዓለም ሳይፈጠር በመለኮቱ ከአብ በተወለደ፣ ዳግመኛም እኛን ለመዳን በኋላ ዘመን ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በእግዚአብሔር ልጅ እናምናለን፤ የቀኑ ቀጠሮ ሲደርስ እግዚአብሔር ልጁን ላከ፣ ከድንግልም ተወለደ፡፡ (ቅዱስ አትናቴዎስ)
  • ከሰው ባሕርይ ጋር አይመሳሰልም፣ ልደቱም እንደ ሰው ልደት አይደለምና ረቂቅ ምሥጢር ነው፤ አይመረመርም፡፡ (ቅዱስ ጎርጎርዮስ)

ምንጭ፡- ሃይማኖተ አበው

ይቆየን

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *