በማኅበረ ቅዱሳን የሩቅ ምሥራቅ ማእከል አባላት ዕለተ አኮቴትን (የምስጋና ቀን) አከበሩ

በሀገር ውስጥና በውጪ ባሉ የማኅበረ ቅዱሳን ሁሉም መዋቅሮች የሚከበረው ዕለተ አኮቴት (የምስጋና ቀን) በሩቅ ምሥራቅ ማእከል ተከብሯል፡፡ ዕለተ አኮቴት በየዓመቱ ከሆሳዕና በዓል ቀድሞ በሚውለው ዕለተ ዐርብ የሚከበር ሲሆን መርሐግብሩ ማኅበሩ በሚያከናውናቸው አገልግሎቶች ውጤታማ እንዲሆን የረዳውን እግዚአብሔርን የሚያመሰግንበት ነው፡፡ መርሐግብሩ በሩቅ ምሥራቅ ማእከል ስር ባሉ የተለያዩ ሀገራት የሚገኙ ወንድሞችና እህቶች በኦንላይን በተገኙበት የተከናወነ ሲሆን በአባቶች ጸሎት ከተጀመረ በኋላ በቀሲስ ሙሉቀን ብርሃኑ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡ ያሬዳዊ ዝማሬዎች ቀርበዋል፡፡ በአገልግሎታቸው አርኣያ ለሆኑ ወንድሞች እና እህቶች የምስጋና መርሐግብር በማእከሉ ሰብሳቢ ዲ/ን አያናው ፀጋ መሪነት የተከናወነ ሲሆን የበለጠ እንዲያገለግሉ አደራ ጭምር የተሰጠበት ነው፡፡ የሩቅ ምሥራቅ ማእከል ፀሀፊ ዲ/ን ፋንታሁን ትኩ የማኅበሩን መልእከት ያስተላለፉ ሲሆን የቤተ ክርስቲያናችን መከራ በየዘመኑ መልኩን እየቀያየረ መጠኑን እያሰፋ እንደመጣ ገልጸዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አካል የሆነው ማኅበረ ቅዱሳን ባለፉት ፴፪ ዓመታት በእግዚአብሔር አጋዥነት በአውሎና በወጀብ ውስጥ አልፎ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎት እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸው ለዚህም አምላካችንን እግዚአብሔርን ልናመሰግን፤ ለቀጣዩ ደግሞ በጸሎትና በአገልግሎት ተግተን በፍቅርና በእንድነት ተባብረን የበለጠ በመሥራት የቤተክርስቲያንን ችግር ለመቅረፍ ሁላችንም በቁርጠኝነት እንድንዘጋጅ አሳስበዋል።