“ለሦስት ቀናት በጾምና በጸሎት በአንድ ልብ ሆነን ወደ ፈጣሪያችንን እንድንጮህ አደራ እንላለን”-ቋሚ ሲኖዶስ

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ የጾምና የምሕላ አዋጅ አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ
የነነዌም ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ ለጾም አዋጅ ነገሩ!
ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ” (ትንቢተ ዮናስ ምዕራፍ 3 ቁጥር 5)
ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በተከሰተው ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና አስተዳደራዊ መዋቅሮቿን በመጣስ መፈንቅለ ሲኖዶስ በማድረግ በሕገወጥ መንገድ ኤጲስ ቆጶስነት ሢመት በሰጡትና በተሾመ ግለሰቦች ላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ጥር 18 ቀን 2015ዓ.ም. ቃለ ውግዘት ማስተላለፉ ይታወቃል።
     ይሁን እንጂ እነዚህ ሕገወጥ ቡድኖች ከድርጊታቸው ሊታቀቡ ካለመቻላቸውም በላይ በመንግሥት ኃይሎች በመታገዝ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምታስተዳድራቸውን መንበረ ጵጵስናዎችንና ቢሮዎችን በኃይል በመውረርና በመስበር ከፍተኛ ጥፋት እያደረጉ ከመሆኑም በላይ የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችን ሠራተኞች ካህናትና ምእመናን በማሰርና በማንገላታት ላይ ይገኛል፡፡
መንግሥትም ሕግ ከማስከበር ይልቅ ለሕገ ወጥ ቡድኖች ድጋፍ በመስጠት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕግና መብት ሊያስከብር ስላልቻለ ሁሉን ማድረግ ወደሚቻለው አምላካችን በመማፀን ጸሎትና ምሕላ ማድረጉ አስፈላጊ መሆኑን ቅዱስ ሲኖዶስ ተረድቷል።በመሆነም ጾመ ነነዌን ምክንያት በማድረግ በመላው ዓለም የሚገኙ ሕዝበ ክርስቲያን ጥቁር ልብስ ብቻ በመልበስ በጾምና በጸሎት ምሕላ በመያዝ በቤተ ክርስቲያን ዓውደ ምሕረት በመገኘት ወደ እግዚአብሔር ጾም፤ ጸሎትና ምሕላ እንድታቀርቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
ጥቁር ልብስ የምንለብሰው በመከራ መጽናት ለመግለጽ ነው፡፡
እንደሚታወቀው ጥቁር የእውቀት ምልክት ነው ተማሪዎች አውቀናል ሲሉ ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፡፡ እኛ ከእውቀት በላይ የሆነውን አምላካችንን በመማፀን ከዚህም ማንም ሊያናውጽን እንደማይችል የምናረጋግጥበት፤ ጥቁር የእውነት ምልከት ነው ዳኞች እውነት እንፈርዳለን ሲሉ ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፡፡ እኛም መከራው የሚያሰቅቀን ሳይሆን ይበልጥ ልንጸናና ልንበረታ የሚገባ መሆኑን ለዓለም ሕዝብ የምናሳይበት በመሆኑ ከጥር 29 እስከ የካቲት 1 ቀን 2015 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በጾምና በጸሎት በአንድ ልብ ሆነን ወደ ፈጣሪያችንን እንድንጮህ አደራ እንላለን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በደረሰባት የውስጥ ፈተና ሀዘኗ ከባድ ነው።” ብፁዕ አቡነ አብርሃም

ብፁዕ አቡነ አብርሃም

ብፁዕ አቡነ አብርሃም

        ብፁዕ አቡነ አብርሃም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ይህን የገለጹት ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጪ የተፈጸመውን “የጳጳስ ሹመት” አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ነው።
         ብፁዕነታቸው እንደገለጹት በፈተና የሚያጸናው ሁል ጊዜ ፈተናዎችን እያሳለፈ ለዘመናት ሲጠብቃት የነበረ እግዚአብሔር ዛሬም ጥበቃውና መግቦቱ እንደማይለያት ሙሉ እምነት አለን። በደረሰው ክስተትም እጅግ አዝነናል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ታዝናለች።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከ3ሺ ዘመን በላይ የራሷን አንድነት ከማስጠበቅ አልፋ የሀገርን አንድነት ስታስጠብቅ ለሰው ልጆች አንድነት ትልቁን ድርሻ በመውሰድ ስትሠራ የኖረች አሁንም ያለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነች በማለት ገልጸዋል።
              ይህንን አንድነቷን የሚንድ ሕጋዊ ሰውነቷን የሚጥስ አላስፈላጊ ክስተት ተፈፅሟል። በዚህም ቅዱስ ፓትርያርኩ በአስተላለፉት ጥሪ መሠረት ከሀገር ውስጥ ከሀገር ውጭ የምትገኙ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከነገው ዕለት ጀምሮ የቅዱስነታቸውን ጥሪ በመቀበል እንድትገኙ በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል።
ብፁዕነታቸው አክለውም የተፈጠረውን ችግር በዝርዝርና በጥናት ቅዱስ ሲኖዶስ አይቶ የመጨረሻውን ውሳኔ እስከሚሰጥበት ጊዜ ድረስ ምእመናንና አገልጋዮች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሁላችሁም በየአላችሁበት ቤተ ክርስቲያንን እንድትጠብቁ ሲሉ አሳስበዋል። ተመሳስለውና የሌለ ሀሳብ እያቀረቡ ሕዝብን ከሚለያዩ ሠዎች እንድትጠበቁና እንድትጠብቁ በጽናት፣ በትእግስትና በፍቅር ሕጋዊ በሆነ ነገር ሁሉ ቤተ ክርስቲያንን እንድትጠብቋት በአንድነቷ የተረከብናትን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በአንድነቷ ለነገው ትውልድ ለማስረከብ የእያንዳንዳችንን ድርሻ እንድንወጣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ብለዋል።
            በመጨረሻም ሕጋዊ ሰውነቷ የተረጋገጠ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በሕጋዊ ሰውነቷ የመጠበቅ የማስጠበቅ ኃላፊነቱ የመንግሥት ስለሆነ ይህን የተፈጸመውን ግፍ መንግሥት ተመልክቶ የቤተ ክርስቲያኗን ሉዓላዊነት በመጠበቅና በማስጠበቅ የራሱን ድርሻ እንዲወጣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪ አቅርበዋል ።

የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና እና የምክክር መርሐ ግር ተካሄደ

በማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ አዘጋጅነት ለማእከላት ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ዋና ክፍል ኃላፊዎች፣ ለመደበኛ አስተባባሪዎች እና በዋናው ማእከል ለግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባሪያ አባላት የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና እና የምክክር መርሐ ግብር ከኅዳር ፫-፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ተካሄደ፡፡

በማኅበሩ መሰብሰቢያ አዳራሽ ለሁለት ቀናት በተካሄደው ሥልጠናም አዲሱን የማኅበሩን ተቋማዊ ለውጥ በተመለከተ በመጋቤ ሀብታት ታደሰ አሰፋ እና አቶ ግዛቸው ሲሳይ ለአንድ ቀን የቆየ የግንዛቤ ማስጨበጫ የዳሰሳ ጥናት ቀርቧል፡፡ በዚህም የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር ውጫዊና ውስጣዊ ከባቢያዊ ሁኔታን መሠረት አድርጎ አሁን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ በማጤን ተቋማዊ ለውጡ እንደተዘጋጀ ተገልጿል፡፡ የማኅበሩ ለውጥ ከየት ወደ የት ትንተና የቀረበ ሲሆን አዲሱ የማኅበሩ ርእይ፣ ተልእኮ፣ ዕሴት እና ዓላማም በተመለከተ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡

በቀረበው ገለጻ መነሻነትም ከተሳታፊዎች የተለያዩ ጥያቄዎች ቀርበው ምላሽ የተሰጣቸው ሲሆን፤ የቡድን ውይይት፣ እንዲሁም ከአገልግሎት ጋር ተያይዞ የልምድ ልውውጥ እና የምክክር መርሐ ግብር ተካሂዷል፡፡

እሑድ በነበረው መርሐ ግብርም “ውጤታማ መሪነት እና የመሪነት ችሎታ፤ Effective leadership & leadership skill” በሚል ርእስ በመጋቤ ሀብታት ታደሰ አሰፋ እንዲሁም “ተግባቦት፤ Communication” በሚል ርእስ በዶ/ር ወርቁ ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ በተሰጡት ሥልጠናዎች ላይ ከተሳታፊዎች ጥያቄዎች ቀርበው በጥናት አቅራቢዎቹ ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

በሥልጠናው ላይ ተሳታፊዎች ከነበሩት አባላት መካከል ቆይታቸውን በተመለከተ ሲገልጹ “ከአቀባበሉ ጀምሮ እስከ ፍጻሜው መልካም ጊዜን አሳልፈናል፡፡ ተቋማዊ ለውጡ ላይ ያለንን ብዥታ ያጠራንበት፣ በሌሎቹም በተሰጡን ሥልጠናዎች በቂ ዕውቀት መጨበጥ ችለናል፡፡ በተለይም ያካሄድናቸው የልምድ ልውውጦች ለአገልግሎት እንድሣሣ እና እንድንበረታ የሚያደርጉን ናቸው” በማለት ገልጸዋል፡፡

በዚህ መርሐ ግብር ከ፴፩ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት የተውጣጡ ፵፫ ተሳታፊዎች የተካፍለዋል፡፡

ቁስቋም ማርያም

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጋር ወደ ግብፅ እንደሚሰደድ ወይወርድ እግዚእነ ውስተ ምድረ ግብፅ እንዘ ይጼዐን ዲበ ደመና ቀሊል፤ ጌታችን በፈጣን ደመና (በእመቤታችን ጀርባ) ተጭኖ ወደ ግብፅ ይወርዳል ብሎ በተናገረው ትንቢት መሠረት ስደትን ለመባረክ፣ የግብጽን ጣኦታት ያጠፋ ዘንድ ተሰዷል፡፡ (ኢሳ. ፲፱፥፩)

ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስም የጌታችንን ስደት በተመለከተ “የእግዚአብሔር መልአክ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ “ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይሻዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱንም ይዘህ ወደ ምድረ ግብፅ ሽሽ፤ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ኑር” በማለት እንደ ጻፈው ቅዱስ ዮሴፍ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ከልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንዲሁም ሰሎሜን ይዞ ወደ ግብፅ ተሰዷል፡፡ (ማቴ. ፪፥፲፫)

ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደ ግብፅ ይሰደዱ ዘንድ እንደነገራቸው ሁሉ ፵፪ ወራት (ሦስት ዓመት ከስድስት ወራት) ሲፈጸም የሄሮድስ መሞት እና ወደ ኢየሩሳሌም ይመለሱ ዘንድ የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሞተዋልና፥ ተነሥተህ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ በማለት ነግሯቸዋል፡፡ (ማቴ.፪፥፲፱-፳፩) በዚህም መሠረት ኅዳር ፮ ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተመለሱበትን ቀን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

ደብረ ቁስቋም በደቡብ ግብፅ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ወደ ግብፅ ከተሰደደች በኋላ አሳዳጅ የነበረው ሄሮድስ በመሞቱ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከስደት ሲመለሱ ያረፉበት ቦታ ነው፡፡ ይህ ቁስቋም ተራራ ጌታችን ብዙ ተዓምራት የፈጸመበት በመሆኑ ተባርኳል፤ ተቀድሷልም፡፡ ይህ ተራራ የተቀደሰ ስለመሆኑ የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ታኦፊሎጎስ በድርሳነ ማርያም እንዲህ ብሏል፤ ይህም ከሀገሮቹ ሁሉ ተራሮች የሚበልጥ (የተለየ) ከፍ ያለ ተራራ ነው፡፡ በውስጡ ቅዱስ አግዚአብሔር ያድራል፡፡ ይህንን ተራራ የእግዚአብሔር ልጅ ወዶታል፤ አክብሮታልምና፤ ከዓለም ሀገሮች ሁሉ ከተቀደሰች እናቱ ጋር አድሮባታልና፡፡ ከመላእክት ቤት ያድር ዘንድ አልወደደም፤ ቢታንያንም አልመረጠም፤ ከተራራው ላይ ባለች ገዳም ቤት ውስጥ አደረ እንጂ፤ ነቢዩ ዳዊት፤ የጽዮንን ተራራ ወደደ፤ በአርያምም መቅደሱን ሠራ” እንዳለ፡፡

ሊቁም በመቀጠል ሙገሳውን እንዲህ ሲል ገልጿል፤ አንተ ተራራ ሆይ የእግዚአብሔር ማደሪያ በሆንህ ጊዜ በኪሩቤልና በሱራፌል መካከል ፍጹም ደስታ ተደረገ፡፡ የመላእክት ሠራዊት ቅዱስ የሆነ ፈጣሪያቸውንና ጌታቸውን ይታዘዙ (ያገለግሉ) ነበር፡፡ አንተ ተራራ ሆይ ያደረብህ ጌታችን ስለሆነ ከተራሮች ሁሉ ከደብረ ሲናም ይልቅ ከፍ ከፍ አልህ፤ ጌታችን በደብረ ሲና ባረፈ ጊዜ ፍጹም ደስታ፣ ታላቅ ብርሃንም በሆነ ጊዜ መቅረብና መመልከት ከሙሴ በቀር የቻለ የለም፡፡ እርሱም ቢሆን ፊቱን ማየት አልቻለም፡፡ ሥጋ ለባሽ ሁሉ እርሱን ዐይቶ በሕይወት መኖር የሚቻለው የለምና፡፡ እኛ ግን አየን፤ ከዚህ ማደሩንም ተረዳን፤ ዳግመኛም ንጽሕት በሆነች በማርያም ዘንድ አየነው፡፡ ቅድስት ከሆነች ከእመቤታችን ማርያም ዘንድ በቤተልሔም ስለ እኛ በተዋሐደው ሥጋ በጨለማና በሞት ጥላ ሥር ያለን እኛን ከቸርነቱና ሰውን ከመውደዱ የተነሣ መጥቶ አዳነን፤ ከዓለም ሁሉ ይልቅ ጣዖትን በማምለክ ሲበድሉም ወደ ግብፅ  ሀገር ወርዶ በእነርሱ ላይ የመለኮትነት ብርሃኑን በማብራት ታላቅ የሆነ ክብሩን ገለጠ፡፡” እመቤታችን ቅድስት ማርያምም ከጌታችን ኢየሱስ ጋር በዚህም ተራራ ስድስት ወራት ዐርፈዋል፡፡ (ድርሳነ ማርያም)

ኅዳር ፮ ቀን የሚነበበው የመጽሐፈ ስንክሳር ክፍል ጌታችን ኢየሱስ ዳግመኛም በኋላ ዘመን ሐዋርያትን በደብረ ቁስቋም ሰብስቦ፤ ታቦትንና ቤተ ክርስቲያኑን አክብሮ የቊርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እንደ ሰጣቸው፤ ጌታችንም ካረገ ከብዙ ዘመናት በኋላ በኅዳር ፮ ቀን አስተጋብኦሙ እግዚእነ ለሐዋርያቲሁ ቅዱሳን ውስተ ዝንቱ ደብረ ቊስቋም ወቀደሰ ታቦተ ወቤተ ክርስቲያን ወሠርዐ ቊርባነ ወመጠዎሙ ሥጋሁ ቅዱሰ ወደሞ ክቡረ፤ በዚህ በደብረ ቊስቋም ቅዱሳን ሐዋርያቱን ሰበሰባቸው፤ ታቦትንና ቤተ ክርስቲያንንም አክብሮ የቊርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ሰጥቷቸዋልይላል፡፡ (ስንክሳር ኅዳር ፮)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ንስሓ አባቶችና የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት

ዲ/ን ኢያሱ መስፍን

የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ወጣቱን ወደ መንፈሳዊ ልዕልና ለማድረስ የሚደረግ ውጣ ውረድ የበዛበት ጉዞ ነው። ለዚህም የጉዞው ተሳታፊዎች እና ጉዞውን የተቃና ለማድረግ ከፊት የሚቀድሙ መሪዎች የአገልግሎት ተነሳሽነትና ቁርጠኝነት ለውጤቱ ማማር ትልቁን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡

በየጊዜው የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎት የሚረከቡ ወጣቶች በሚኖራቸው ዕውቀት፣ መረዳት እና ትጋት ልክ አገልግሎቱን ለማስኬድ እንዲሁም ከታለመለት ግብ ለማድረስ መጣራቸው አያጠራጥርም። እነዚህ ወጣቶች ዕቅዶቻቸውን ለማስፈጸም ከሚደረግላቸው መዋቅራዊ ድጋፍ ባለፈ ጽኑ የሆነ መንፈሳዊ እገዛ ያስፈልጋቸዋል። ይህንን እገዛ ደግሞ መስጠት የሚችሉት የንስሓ አባቶች ናቸው

ወደ አንድ ተራራ የሚወጣ ሰው መውጫ መንገዱን በሚገባ የሚያውቅ መሪ ማግኘት ግድ ይለዋል። የንስሓ አባቶችም ድርሻ ይህን የመሪነት እና የመንገድ ጠቋሚነት ሚና መጫወት ነው፡፡ ከዚህ ማስተዋል እንደሚቻለው በንስሓ አባትነት የሚሾሙ ካህናት ኑዛዜ ተቀብለው የኃጢአት ሥርየትን ከማሰጠት ባለፈ የመንፈስ ልጆቻቸውን በምግባር እና በሃይማኖት ወደ ድኅነት ጎዳና የመምራት ሥራን ይሠራሉ።

ማንኛውም መንፈሳዊ ሥራ በዕውቀትና በችሎታ ላይ በተመሠረተ የራስ መተማመን መነሻነት ብቻ ሊከወን አይችልም፡፡ “እግዚአብሔር ቢፈቅድ ብንኖርም ያን ወይም ይህን እናደርጋለን” ተብሎ የታቀደን ዕቅድ ለመፈጸም በሚደረግ ጥረት ውስጥ የእግዚአብሔርን እገዛ ትልቅ መሣሪያ አድርጎ መጠቀም ግድ ይላል። (ያዕ. ፬፥፲፭)

የንስሓ አባቶችም ይህ አገልግሎት ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጪ የሚፈጸም እንዳይሆን የመምራትና የማስፈጸም ትልቅ ድርሻ አላቸው። ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን ለመቃኘት ያህል፦

. ከመንፈሳዊ ዝለት ማንቃት

የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ከትምህርታቸው ጎን ለጎን በሚኖራቸው ጊዜ በጋራ የሚፈጽሙት አገልግሎት እንደመሆኑ ትዕግሥትን እና ብዙ ጥረትን ይጠይቃል። ነገሮች በተፈለገው ልክ እና ሁኔታ ያለመሄድ ዕድላቸው ሰፊ ከመሆኑ የተነሣ በግለሰቦች ላይ በሚኖር የአገልግሎት ጫና፣ በመርሐ ግብሮች አለመሳካት፣ በቦታ፣ በጊዜ እና በመሳሰሉ ሁኔታዎች አለመመቻቸት ምክንያት በግቢ ጉባኤ አገልግሎት ተሳታፊ በሆኑ ተማሪዎች ዘንድ መባከንን ልናስተውል እንችላለን፡፡ ይህም እንደ አልዓዛር እኅት ማርታ ከአገልግሎት መብዛት የተነሣ መባከን (ሉቃ.፲፥፵) እና ከቃለ እግዚአብሔር እንዲሁም ምሥጢራትን ከመካፈል መራቅ ሊያጋጥሙ የሚችሉ ችግሮች ናቸው።

እነዚህን ችግሮች በመፍታት በኩል ከንስሓ አባት የተሻለ አቅም ያለው አካል ማግኘት አይቻልም። በግቢ ጉባኤው ውስጥ አገልግሎት በመስጠት ላይ ያሉ አባቶች የንስሓ ልጆቻቸው ያሉባቸውን ፈተናዎች ከማንም በተሻለ ያውቃሉና ችግሮቹ ላይ ያተኮሩ የመፍትሔ ሥራዎችን ለመሥራት ትልቁን ድርሻ የመወጣት አቅም አላቸው። በአገልግሎት ላይ ያሉ ተማሪዎች ተስፋ እንዳይቆርጡ በማጽናት፣ በአገልግሎት በመባከን ከሚመጣ መንፈሳዊ ዝለት ከምሥጢራት ሲርቁ እግዚአብሔርን አብነት አድርገው ‘ወዴት አለህ’ (ዘፍ. ፫፥፱) ብሎ መጥራት፣ መፈለግና ማጽናት ይጠበቅባቸዋል፡፡

. እግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት ያለው አገልግሎት እንዲፈጽሙ ማስቻል

ቃየን ወንድሙን በመግደል በደል በፈጸመ ጊዜ ፈታሔ በጽድቅ ከሆነ እግዚአብሔር የተፈረደበት ፍርድ ተቅበዝባዥ መሆን ነው። (ዘፍ. ፬፥፲፪) ሊቃውንት አባቶቻችን “ምድርንም ባረስክ ጊዜ እንግዲህ ኃይሏን አትሰጥህም” የሚለውን ኃይለ ቃል መነሻ አድርገው   ተቅበዝባዥነትን በከንቱ መድከም፣ ጀምሮ አለመፈጸም፣ ዘርቶ ፍሬ ማጣት መሆኑን በትርጓሜአቸው አስረድተውናል። የግቢ ጉባኤ አገልጋዮች ድካማቸው ከንቱ አገልግሎታቸውም ፍሬ አልባ እንዳይሆን ዘወትር ራሳቸውን በጸሎት በማነጽ፣ በንስሓ ማንጻት እና ማዘጋጀት ግድ ይላቸዋል።

የንስሓ አባቶች ንስሓን የመቀበል እና የመናዘዝ አገልግሎት ደግሞ በሌላ በማንም ሊተካ የማይችል ነው። በመሆኑም በግቢ ጉባኤ አገልግሎት ተሳታፊ የሆኑ ተማሪዎችን በመናዘዝ እና ከኃጢአት እንዲነጹ በማድረግ ለአገልግሎቱ መሳካት የበኩላቸውን አባታዊ ኃላፊነት ሊወጡ  ይገባቸዋል።

. የአገልግሎቱን ቀጣይነት ማረጋገጥ

የግቢ ጉባኤ አገልጋዮች በእያንዳንዱ የአገልግሎት እርምጃቸው የንስሓ አባቶቻቸውን ተሳታፊዎች ቢያደረጓቸው ከአገልግሎታቸው መሳካት ባለፈ ከእነርሱ በተጨማሪ ሌሎች አገልጋዮች በሚመጡበት ጊዜ የግቢ ጉባኤን አገልግሎት የተረዱ እና አዲሶቹን አገልጋዮች በተሻለ ጎዳና መምራት የሚችሉ አባቶችን ማፍራት ይቻላል። ይህም የማእከላትን ጫና ከመቀነስ ባሻገር አዳዲስ አገልጋዮች አገልግሎቱን ከታች ከመጀመር ይልቅ በየአጥቢያቸው ያሉ የንስሓ አባቶቻቸውን በማማከር ከነበረበት የማስቀጠል እና የማሳደግ ዕድል እንዲያገኙ ያደርጋል።

ተግዳሮቶች

የግቢ ጉባኤያትን አገልግሎት መረዳት የሚችሉ እና ወርደው ከተማሪዎች ጋር ለመሥራት የመንፈስ ዝግጁነት ያላቸው የንስሓ አባቶች ያስፈልጉናል። የንስሓ አባቶች እና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ቁጥር አለመመጣጠን፣ እስከ አለመግባባት የሚያደርስ ሰፊ የዕድሜ ልዩነት መኖር፣ ለረጅም ጊዜ በገዳማዊ ሕይወት ያለፉ መነኮሳት ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች አባት ሆነው መመደባቸው፣ የቋንቋ ክፍተት መኖሩ፣ ዘመኑን ዋጅቶ በሚገባው ልክ ወጣቱን ለማስተማር እና ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማቅረብ የሚያስችል የትምህርት ዝግጅት የሌላቸው አባቶች በንስሓ አባትነት መመደባቸው እና የመሳሰሉት ምክንያቶች የንስሓ አባቶች በሚፈለገው መጠን በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ውስጥ የሚጠበቅባቸውን በጎ አስተዋጽኦ እንዳያበረክቱ እንቅፋት ሆነዋል።

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የእረኝነት ሥራን የሚሠሩ እነዚህ ካህናት ትሩፋትን እና ትጋትን ገንዘብ ያደረጉ፣ በመንፈስ ብርታት፣ በትምህርተ ሃይማኖት ብስለት እና በተቀደሰ ሕይወት ይጠብቋቸው ዘንድ ከተሾሙላቸው ሰዎች እጅግ ተሽለው መገኘት እንዳለባቸው ሲያስረዳ “በካህኑና በምእመናኑ መካከል ሊኖር የሚገባው ልዩነት አእምሮ ባለው ሰው እና ደመ ነፍሳዊ በኾኑ እንስሳት መካከል ያለውን ያህል የሰፋ ሊሆን ይገባል። የጉዳዩ ክብደት እና አሳሳቢነት እጅግ ታላቅ ነውና” ይላል። የዚህ ዓይነት ጥንቃቄ በተለይ ዘመን በወለዳቸው አምላክ የለሽ እሳቤዎች እና ፍልስፍናዎች፣ በምንፍቅና ትምህርቶች፣ በሰፋፊ የኃጢአት ልምምዶች እና በመሳሰሉት ለመነጠቅ የሰፋ ዕድል ላላቸው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች አባት ሆነው የሚሾሙ ካህናትን በተመለከተ ሲሆን ይበልጥ ምክንያታዊ ይሆናል።

የመፍትሔ ሐሳቦች

የንስሓ አባቶች ኑዛዜን ተቀብሎ ከኃጢአት እሥራት ከመፍታት ባለፈ በግቢ ጉባኤ አግልግሎት ውስጥ ጠለቅ ያለ ተሳትፎ እና የእረኝነት ድርሻ እንዳላቸው መረዳት ይገባቸዋል፡፡ በግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ላይ ያሉ ወጣቶችም ዝግጅት ያላቸውን የንስሓ አባቶች የመንፈስ ልጆቻቸውን በተመለከተ በሚወሰኑ ውሳኔዎች እና በሚሠሩ ሥራዎች ላይ ንቁ ተሳታፊዎች እንዲሆኑ ሁኔታዎችን ማመቻቸት ያስፈልጋል። በመሆኑም በንስሓ አባቶችና በልጆቻቸው መካከል ያለውን ግንኙነት የተከሳሽ እና የዳኛ አስመስሎ የሚያሳየውን ምዕራባዊ ነጽሮት በማራቅ ኦርቶዶክሳዊ በሆነው የሐኪም እና ታካሚ ዓይነት ግንኙነት እሳቤ መነሻነት ጥብቅ የሆነ መረዳዳት እና መግባባት ላይ የተመሠረተ ግንኙነት መፍጠር መቻል ያስፈልጋል፡

ማእከላት እና የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላትም ግቢ ጉባኤያቱ በያሉባቸው አካባቢዎች የሚነገሩ ቋንቋዎችን እና የአካባቢውን ባህል የተረዱ ካህናትን ከዚያው አካባቢ እንዲገኙ በማድረግ በየደረጃው ያሉ መሠረታዊ ችግሮችን ለመቅረፍ ሊሠሩ ይገባል። በተጨማሪም አገልግሎታቸው ንስሓን ከመቀበል ያለፈ እና ሁለንተናዊ የመንፈሳዊ አባትነት አገልግሎት መሆኑን ተረድተው በግቢ ጉባኤያት አገልግሎቶች ውስጥ የበኩላቸውን እንዲወጡ ማንቃትና ይህንን ማድረግ እንዲችሉ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡

ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት

ዓለማየሁ ገብሩ

ትውፊት ማለት አወፈየ ከሚለው የግእዝ ግሥ የመጣ ሲሆን ውርስ፣ ቅብብል ተብሎ ይተረጎማል፡፡ ትውፊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ትምህርቶቿን ጠንቅቃ ከያዘችበት እና ልጆቿንም ከምትመራባቸው ሦስቱ የመሠረተ እምነት ምንጮች ውስጥ አንደኛው ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት ተብለው የሚጠቀሱት፡- ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊት ሲሆኑ እነዚህ መሠረቶች ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሳትለወጥና ሳትበረዝ እንደ ደመቀች ከትውልድ ወደ ትውልድ እንድትተላለፍ አድርገዋታል፡፡

ለቤት መቆም ብቻ ሳይሆን ቤቱ ዕድሜ እንዲኖረውም የሚያደርገው የመሠረቱ ጥንካሬ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ትውፊት አንድ ሰው ከእርሱ በፊት ከነበረው ማኅበረሰብ የሚቀበለውና የሚወርሰው እምነት፣ ባህል፣ የአኗኗር ዘይቤ፣ …ወዘተ ሲሆን ሒደቱም በዚህ ሳያበቃ እርሱም በተራው ለተተኪው የሚያስተላልፈው ነው፡፡

ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ ስለ ትውፊት እንዲህ በማለት ማብራሪያ ይሰጣሉ፡-“ትውፊት በቃል ወይም በጽሑፍ ወይም በተግባር እንቅስቃሴ ከአንዱ ወደ ሌላው የሚተላለፍ ታሪክ፣ ትምህርት፣ ባህል፣ ወግና ሥርዓት ነው፡፡ ትውፊት በተጨባጭ በትክክል የተፈጸመ እንጂ ተረት አይደለም፡፡ ከሕገ ልቡና ወደ ሕገ ኦሪት፣ ከሕገ ኦሪት ወደ ሕገ ወንጌል፣ በቅብብሎሽ የመጣ የተወረሰና ለተከታዩ ትውልድ የተላለፈ ነው፡፡ ትውፊት ልማደ ሀገርን ሕገ እግዚአብሔርን ባህለ ሃይማኖትን ሁሉ የሚያጠቃልልና እንደ መንፈሳዊ ሕግ ሆኖ ሊያዝ የሚችል ነው፡፡” ይላሉ (ሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ፤ ፈለገ ጥበብ መጽሔት ፪ኛ ዓመት ቁጥር ፲፭/፲፱፻፺፪ ዓ.ም. ገጽ ፲፭)

ትውፊት ከትውልድ ወደ ትውልድ በሦስት መንገዶች የሚተላለፍ ሲሆን፤ እነርሱም፡- የሚዳሰስ፣ የማይዳሰስ እና በቃል ይተላለፋሉ፡፡

ሀ. በሚዳሰስ መንገድ የሚተላለፍ ትውፊት፡-

በሚዳሰስ መንገድ የሚተላለፍ ትውፊት በሆነ ዘመን ተሠርተው አገልግሎት የሚሰጡ አብያተ ክርስቲያናት፣ ንዋየተ ቅድሳት እና ቅዱሳት መጻሕፍትን የመሳሰሉት ቅርጻቸውንና ይዘታቸውን ሳይለውጡ ከትውልድ ወደ ትውልድ ተጠብቀው የሚተላለፉበት የትውፊት መተላለፊያ መንገድ ነው፡፡ እነዚህ ንዋያተ ቅዱሳት በክብር እየተጠበቁ ወደ ቀጣይ ትውልድ ይሸጋገራሉ፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን በትውፊት ምክንያት የሚነቅፉና ትውፊት አያስፈልግም መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ የሚሉ ሰዎች መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ በትውፊት ያለንበት ዘመን መድረሱን ይዘነጋሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ መቼ መዘጋጀት ጀመረ? ከሚለው አንስቶ መቼ አሁን ያለበትን ቅርጽ ያዘ እስከሚለው ድረስ ያለውን ብንመረምር ከአንዱ ወደ አንዱ እየተላለፈ በትውፊታዊ መንገድ ቀድሞ የተጻፉትን በመቀበል በየዘመናቱ የሚጻፉትንም ደግሞ በማካተት አሁን ያለበትን መልክ ይዞ እኛ ጋር እንደደረሰ መዘንጋት የለብንም፡፡

ለ. በማይዳሰስ መንገድ የሚተላለፍ ትውፊት፡-

ርእያዊ ትውፊት ሲባል የተለያዩ ባህሎች አከባበር፣ የተለያዩ መንፈሳዊ መዝሙራት ወይም ወረብ አቀራረብ እንዲሁም መንፈሳዊ አለባበስና አመጋገብ የመሳሰሉ በማየት የምንወርሳቸው ወይም የምንቀበላቸው የትውፊት ዓይነቶች ናቸው፡፡ ለዚህ ጥሩ ማሳያ የሚሆነው በሕገ ልቡና ዘመን የአሥራት በኲራት አቀራረብ ሕግ ሆኖ ለሙሴ ከመነገሩ በፊት አበ ብዙኃን አብርሃም፣ ልጁ ይስሐቅና ያዕቆብ ያቀርቡ ነበር፡፡ የመሥዋዕትንም አቀራረብ በማየትና በመስማት ከልጅ ልጅ እየተቀባበሉ ሲገለገሉበት ነበር፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ አሥርቱን ትእዛዛት ከመቀበሉ በፊት ቅዱስ ዮሴፍ ዝሙት ኃጢአት እንደሆነና ከዚያም ሲሸሽ የዝሙት ኃጢአት እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ኃጢአት መሆኑን ዐውቆ ራሱን ሲጠብቅ እናየዋለን (ዘፍ.፴፱፤፱)፡፡ ሕግ ሳይሰጥ ከየት ዐወቀው ከተባለ ከአባቶቹ በማየትና በመስማት የተማራቸው ነገር ስላለ ነው፡፡  እስራኤላውያን የፋሲካል በዓል አከባበር አሁን ድረስ ጥንታዊ ባህሉን ጠብቀው ያከብራሉ፡፡ በዓል አከባበሩ ተጽፎላቸው ሳይሆን በማየት ብቻ ከአንዱ ትውልድ ወደ አንዱ ትውልድ እየተላለፈ የመጣ ስለሆነ ነው፡፡

በአጠቃላይ ትውፊት የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ወጥ ሥርዓት እንዲኖራት የሚረዳ ሲሆን ከዚህ ትውፊታዊ ሥርዓት የሚወጡትን ደግሞ ለይተን እንድናውቅበት ይረዳናል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለን “ዳሩ ግን ማንም ሊከራከር ቢፈቅድ እኛ ወይም የእግዚአብሔር አብያተ ክርስቲያናት እንዲህ ያለ ልማድ የለንም ” (፩ቆሮ.፲፩፤፲፮) በማለት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ውጪ ካሉ ተቋማት እንድንጠበቅ እንዲሁም ሥርዓት፣ ወግ፣ ባህል ከሌላቸው አካላት ጋር መለየታችንን በጉልህ የሚያሳየን መሠረተ እምነት ነው ትውፊት፡፡

ሐ. ቃላዊ ትውፊት፡-

ቅዱስ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ሰዎች ሲያስተምር “አሁንም ወንድሞቻችን ሆይ ጸንታችሁ ቁሙ፤ በቃላችንም ቢሆን ወይም በመልእክታችን ያስተማርናችሁንና የሠራንላችሁን ሥርዓት ያዙ፡፡” (፪ተሰ.፪፥፲፭) ይላል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ከጻፈልን ፲፬ቱ መልእክት በተጨማሪ በቃል የሰበከውንም እንድንይዝ ይመክረናል፡፡ እንደሚታወቀው የክርስቶስ ቤተሰብ የተባሉት ከዋለበት ውለው፣ ካደረበትም አድረው ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብለው ከተማሩት ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ሁለቱ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ዮሐንስ እንዲሁም ከሰባ ሁለቱ አርድእት ደግሞ ቅዱስ ማርቆስና ቅዱስ ሉቃስ ብቻ ናቸው ወንጌልን የጻፉልን፡፡

የተቀሩት ሐዋርያትና አርድዕት የእግዚአብሔርን ቃል አላስተማሩም? አልሰበኩም? አልጻፉም ማለት ነው? አይደለም፡፡ ይህ የሚያሳየው ከላይ ባነሣነው የቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት መሠረት ባይጽፉም ወንጌል መስበካቸውን አንጠራጠርምና በቃል የሰበኩትንም እንድንይዝ ተነግሮናል፡፡ ለዚህም ነው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ቅዱሳን ሐዋርያት በቃል የሰበኩትን የእነሱ ተከታይ የሆኑና ደቀ መዛሙርቶቻቸው ጽፈው ያስተላለፉትን የምትቀበለው፡፡

ኦርቶዶክሳዊ ቃላዊ ትውፊት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ያስተማራቸውን፣ ሐዋርያትም ለተከታዮቻቸው ያስተላለፉትን እየተቀባበሉ እዚህ እኛ ዘመን ላይ ደርሷል፡፡ “ለእናንተ ደግሞ አሳልፌ የሰጠሁትን እኔ ከጌታ ተቀብያለሁና” (፩ቆሮ.፲፩፥፳፫) እንዲል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፡፡

ቃላዊ ትውፊት ከጥንት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን በኩል ቃል በቃል ሲነገር የመጣ በቃልም በጽሑፍም ከአበው ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የኖረና የሚኖር ነው፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት ያልተጻፉትን ከአበው ቃል በቃል የተላለፉትን የእምነት፣ የሥርዓት፣ የትምህርትና የታሪክ ውርሶች የሚቀርብበት ነው፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት በቃላዊ ትውፊት አማካይነት በወንጌል ያልተጻፈውን የጌታችን ትምህርት ጌታችን የተናገረው ብለው መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሲጽፉ እናያለን፡፡ ለምሳሌ “ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፀዕ ነው፤ ያለውንም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቃል ዐስቡ፡፡” (ሐዋ.፳፥፴፭) ይላል፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አለ ያለውን ቃል በአራቱም ወንጌል ውስጥ ተጽፎ አናገኘውም፡፡ ከየት አመጣው ብንል ጌታችን ሲያስተምር የሰማውን እንደጻፈ መረዳት ቀላል ነው፡፡

ጌታችንስ በወንጌል ከተጻፉት ውጪ ሌላ ቃል አላስተማረም ብሎ ማሰብ ሞኝነት አይደለምን? ወንጌላውያኑስ ጌታ የተናገረው ሁሉን ጽፈዋል ብሎ ማመኑ አይከብድምን? ስለዚህ አራቱ ወንጌላውያን ያልጻፉት ወይም ያልመዘገቡት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርቶች መኖራቸውን መገንዘብ ይገባል፡፡ ለምሳሌ፡- ተረፈ ወንጌል የሚባሉት እንደ ተአምረ ኢየሱስ፣ ድርሳነ ማኅጠዊ ባሉት ተጽፏ፡፡ ለዚህም ነው ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ “ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ” (ዮሐ.፳፥፴) ያለው፡፡

በተጨማሪም ቅዱስ ጳውሎስ “የታያቸውም እንዲህ ግሩም ነበር፤ ሙሴም እንኳን እኔ ፈርቻለሁ ደንግጫለሁም” ብሎ ጽፎልን እናገኛለን (ዕብ.፲፪፥፳፩)፡፡ ነገር ግን ሊቀ ነቢያት ሙሴ አለ ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ የጻፈልንን ቃል ሙሴ በየትኛውም መጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ ጽፎት አናገኝም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ከየት አመጣው? ካልን በቃል በተላለፈ ትምህርት አግኝቶት ነው፡፡

በተመሳሳይ ቅዱስ ጳውሎስ ሙሴን ስለተቃወሙትና ስለተከራከሩት ሁለቱ ጠንቋዮች ሲናገር የጠንቋዮቹን መጠሪያ ስም “ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደተቃወሙት” በማለት ይጠቅሳል፡፡ (፪ጢሞ.፫፥፰)፡፡ ይህ ታሪክ በተመዘገበበት በኦሪት ዘጸ. ፯፥፲፩ ላይም ሆነ በሌላ የኦሪት መጽሐፍት ላይ የእነዚህ ሁለት ጠንቋዮች ስም የተገለጸበት ቦታ የለም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ግን ከነስማቸውን ጠቅሶ ይነግረናል፡፡ ከየት አምጥቶት ስማቸውን ጻፈ ብንል በቃላዊ ትውፊት በተላለፈ ትምህርት መሆኑን እንረዳለን፡፡

የሐዋርያትን የቃል ስብከት በተመለከተ የሚናገሩት ቃል የእግዚአብሔርን ቃል እንጂ ከራሳቸው አመንጭተው እንዳልሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲነግረን እንዲህ ይላል፡፡ “ስለዚህም የመልእክትን ቃል እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ከእኛ በተቀበላችሁት ጊዜ በእውነት እንዳለ በእናንተ በምታምኑ ደግሞ እንደሚሠራ እንደ እግዚአብሔር ቃል እንጂ እንደ ሰው ቃል አድርጋችሁ ስላልተቀበላችሁት እኛ ደግሞ እግዚአብሔርን ሳናቋርጥ እናመሰግናለን” (፩ተሰ. ፪፤፲፫)፡፡

“ጐልማሶች ሆይ፥ ክፉውን ድል ነሥታችሁታልና እጽፍላችኋለሁ” /፩ኛ ዮሐ. ፪፥. ፲፫/፡፡

በጥበበ ሲሎንዲስ

ቅዱስ ዮሐንስ “ጐልማሶች ሆይ፥ ክፉውን ድል ነሥታችሁታልና እጽፍላችኋለሁ” በማለት ክፉውን ዓለም ድል የነሡትን ጐልማሶች ያሞግሳቸዋል፡፡ ይህም በክፉ ዓለም እየኖሩ ክፉውን ማሸነፍ መንፈሳዊ ጥንካሬንና ድል መንሣትን ያመለክታል፡፡ አንዳንድ ወጣቶች ‘በወጣትነት ዘመን ላይ እየኖሩ ቅዱስ መሆን እንዴት ይታሰባል? በዓለም እየኖሩ ጻድቅ መሆን እንዴት ይሞከራል?’ ይላሉ፡፡ ነገር ግን በክፉው ዓለም ኖረው ዓለምን ድል መንሣት እንደሚቻል ከጐልማሳው (ወጣቱ) ዮሴፍ ታሪክ እንማራለን፡፡

ዮሴፍ በገዛ ወንድሞቹ ተሸጦ፣ ከሀገሩ ከነዓን ርቆ በግብፅ ባርነት ሲኖር የመጣበትን ፈተና በመቋቋም ክፉን ድል ነሥቷል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “የጌታው ሚስት ዐይኗን ጣለችበት፤ አፍ አውጥታም፣ ‘አብረኸኝ ተኛ’ አለችው”(ዘፍ. ፴፱፥፯)፡፡  ልትይዘውም በሞከረች ጊዜ ዮሴፍ  “እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? በእግዚአብሔር ፊት እንዴት ኃጢአትን እሠራለሁ?” በማለት ልብሱን ጥሎላት እንደሸሸ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ /ዘፍ. ፴፱፥፰-፱/፡፡

ዮሴፍ እንዲህ ዓይነት እርምጃ መውሰዱ ከፍተኛ ዋጋ አስከፍሎታል። የጲጥፋራ ሚስት ልትበቀለው ፈለገች። በመሆኑም ወዲያውኑ እየጮኸች አገልጋዮቹን መጣራት ጀመረች። ዮሴፍ ሊደፍራት እንደሞከረና እርሷ ስትጮኽ ሸሽቶ እንዳመለጠ ነገረቻቸው። ዮሴፍን ለመወንጀል ባሏ እስኪመለስ ድረስ ልብሱን ይዛ ቆየች። ጲጥፋራ ወደ ቤት ተመልሶ ሲመጣ ያንኑ ውሸት ደግማ ተናገረች፤ ጲጥፋራ ይህን ባዕድ ሰው ወደ ቤት በማምጣቱ ለደረሰባት ነገር ተጠያቂው እርሱ እንደሆነ በተዘዋዋሪ ገለጸች። ጲጥፋራም ተቆጣ፡፡ ዮሴፍም ወደ ወኅኒ ተጣለ፡፡ የጲጥፋራ ሚስት አሳዛኝ ታሪክ እንዲህ ያለውን ክፋት አስከትሎአል፡፡

ዮሴፍ ግን ለራሱም፣ ለአለቃውም፣ ለፈጣሪውም የታመነ መሆኑን በተግባር አስመሠከረ፡፡ የዛሬ ወጣቶች ለምንሠራበት ተቋም፣ ለአለቃችን፣ ለጓደኛችን ታማኞች ነን? የአደራ ጥብቅነት ከሰማይ ርቀት ጋር ተነጻጽሮ በሚነገርበት ማኅበረሰብ መካከል አድገን ታማኞች መሆን አለመቻላችን ምክንያቱ ምን ይሆን? ዮሴፍ ዓለም በኃጢአት ስትፈትነው በወጥመዷ ላለመያዝ እግዚአብሔርን አስቧልና በሐሰት ወንጅለውና ወደ ወህኒ እንዲጣል አድርገው ለመከራ በዳረጉት ጊዜ እግዚአብሔር እርሱን አሰበው፡፡ ስደተኛው ዮሴፍ የግብፅ ሹመኛ ሆነ፡፡ እኛም “መንገዴንና አካሄዴን እንደ ቃልህ አቅና፤ ኀጢአትም ሁሉ ድል አይንሳኝ፡፡” ብለን እንጸልይ /መዝ.፻፲፰፥፻፴፫/፡፡

የወጣትነት ዘመን የብርታት ዘመን ነው፡፡ አባቶቻችን ‘በወጣትነት የለቀሙትን እንጨት በስተርጅና ይሞቁታል’ ይላሉ፡፡ የወጣትነት ዕድሜ ሰው ሠርቶ ማግኘት፣ ወድቆ መነሣት የሚችልበት ወቅት ነው፡፡ “አንተ ጐበዝ፥ በጒብዝናህ ደስ ይበልህ፥ በጒብዝናህም ወራት ልብህን ደስ ይበለው፥ በልብህም መንገድ፥ ዐይኖችህም በሚያዩት ሂድ፤ ዳሩ ግን ስለዚህ ነገር ሁሉ እግዚአብሔር ወደ ፍርድ እንዲያመጣህ ዕወቅ፡፡ ሕፃንነትና ጒብዝና፥ አለማወቅም ከንቱ ናቸውና ከልብህ ቊጣን አርቅ፥ ከሰውነትህም ክፉ ነገርን አስወግድ፡፡” እንዲል (መክ. ፲፩፥፱-፲)፡፡

ወጣትነት ብዙ ተስፋ ያለው የሕይወት ክፍል ነው፡፡ በአንድ ዕድል አለመሳካት እንደገና ከመሞከር አይቆጠብም፡፡ ወጣትነት ደስ ይላል፤ ሲያዩት ያምራል፡፡ ምንም ዓይነት ሰው ሠራሽ መዋቢያዎችን ባይጠቀሙም ወጣትነት ውበት ነው፡፡ ደግነትና ክፋት ግን ምርጫ ነው፡፡ ኃጢአትን የሚያስጥለን ዕድሜ ሳይሆን የእግዚአብሔር ፍቅር ነው፡፡ ራስን፣ ታሪክን፣ ሀገርን፣ ሕዝብን ለመለወጥ የሚያስፈልገው ትልቅ ዕድሜ ሳይሆን ትልቅ ልብ ነው፡፡ ዋናው ብዙ ዘመን መቆየታችን ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ መኖራችን ነው፡፡ ባለን ጥቂት ዘመን ለዘመን የሚተርፍ፣ ለትውልድ የሚነገር ነገር መሥራት ይቻላል፡፡

ወጣትነት እንደ እሳት ብርቱ ነው፡፡ ይህ እሳት በአዎንታዊ መንገድ ሲገለጥ ተነሣሽነትን፣ ትኩስነትን፣ ባለ ራእይነትን ያመለክታል፡፡ ይህ እሳት በአሉታዊ መንገድ ሲገለጥ ደግሞ ቍጣን፣ ችኩልነትን፣ አለመታገሥን፣ ስሜታዊነትን፣ ንዴትን ማለትን ያመለክታል፡፡

እሳት በረከት እንደሆነ ጥፋትም ሊሆን ይችላል፡፡ የሚጠቅሙ ነገሮች በአግባቡ ካልተያዙ የሚያጠፉት የጥቅማቸውን ያህል ነው፡፡ እሳት ሆነው ለመጡብን ውኃ ሆነን ማብረድ ይገባል፡፡ በሥጋ መሻት፣ በፍትወት ልብ ሲመጡብን በቅድስና፣ በፈሪሃ እግዚአብሔር ማብረድና ወደ ንስሓ መጋበዝ ይገባናል፡፡ እሳትነታችን የሚያበስል እንጂ የሚያሳርር እንዳይሆን ውኃነታችንም የሚያመጣጥን እንጂ የሚያጠፋ እንዳይሆን መገምገም አለብን፡፡ “እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ ትጸልዩም ዘንድ በመጠን ኑሩ” እንዲል (፩ኛ ጴጥ. ፬፥፯)፡፡

በመጠን መኖር የኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ጠባይ ነው፡፡ ይኸውም “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣህን ዐስብ” የሚለውን መመሪያ ለመጠበቅ ይጠቅማል (መክ.፲፪፥፩)፡፡ ፈጣሪው እግዚአብሔርን የሚያስብ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት ሰው የሚከፋበትን አይናገርም፣ በሰዎች መካከል መለያየትን አይፈጥርም፣ ወላጆቹን አያሳዝንም፣ ጎረቤቶቹን አያውክም፣ ምስኪኖችን አያሳቅቅም፣ የሰዎችንም ክብር አይነካም፡፡

ልበ አምላክ ዳዊት “ጐልማሳ መንገዱን በምን ያቀናል? ቃልህን በመጠበቅ ነው፡፡” በማለት እንደተናገረ (መዝ. ፻፲፰፥፱) ጐልማሶችን በቃለ እግዚአብሔር እንዲበረቱ ማስተማርና መንገድ መምራት ያስፈልጋል፡፡ ወጣቶች ንግግር ስለተማሩ፣ ገንዘብ አያያዝ ስላወቁ፣ የምስክር ወረቀት ስለያዙ ብቻ የሕይወት ብስለት አላቸው ማለት አይደለም፡፡ በታላላቅ ተቋማት ስለሠሩም ታላቅ ሆኑ ማለት አይደለም፡፡ ስለዚህ ታዋቂዎች ብቻ እንዲሆኑ ጥረት ከማድረግ ይልቅ አዋቂዎች እንዲሆኑ ማገዝ ይገባል፡፡ ለዚህም ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ “የእግዚአብሔር ቃልም በእናንተ ዘንድ ጸንቶ ይኖራልና” በማለት እንደተናገረው ከሥጋዊ አስተሳሰብና ድርጊት ርቀው የእግዚአብሔርን ቃል የሕይወት መመሪያቸው አድርገው እንዲጓዙ መርዳት ያስፈልጋል፡፡

በልጅነታችን ጭቃ አቡክተን እንጫወት ነበር፡፡ በዚያም ደስ ይለን ነበር፡፡ ካደግን በኋላ ግን ጭቃን እንኳን በእጃችን ልንነካው በእግራችን ልንረግጠው እንጸየፈዋለን፡፡ ምክንያቱም ማደግ ያስገኘልን ዕውቀት ከጭቃ ከመቆሸሽ በቀር ምንም አይገኝም የሚል ነው፡፡ እንዲሁም በአእምሮ ሕፃን በነበርንበት ዘመን በኃጢአት ለመደሰት ሞክረናል፡፡ ተደልለንም አልፈናል፡፡ ለመንፈሳዊ አካለ መጠን ስንደርስ ግን ከኃጢአት ከመርከስ በቀር ምንም እንደማይገኝ ይገባናል፡፡ ደግሞም ኃጢአትን ልንተው የሚገባን ቅጣቱን ማለትም በሥጋ እስር ቤትን፣ በነፍስ ገሀነመ እሳትን ፈርተን ብቻ ሳይሆን የንጹሐ ባሕርይ እግዚአብሔር ክቡር ፍጥረት ነኝ፣ የክርስቶስ ተከታይ ክርስቲያን ነኝ፣ የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ቤተ መቅደስ ነኝ ብለን መሆን አለበት፡፡

በተረፈ ወጣቶች ሆይ! እናንተ ያወቃችሁት በዓለም ላይ ያለው ብቸኛ ዕውቀት አይደለምና፣ ደግሞም ዕውቀት በየዘመኑ ያድጋልና ሌሎችን ለመስማት ፈቃደኛ ሁኑ፡፡ እስከ ዘለዓለም የምንማር ነንና በሃያና በሠላሳ ዓመት ዕውቀትን ጠነቀቅናት ብላችሁ አታስቡ፡፡ በኃይል ሁሉን እቀይራለሁ ከሚል አስተሳሰብ ውጡ፡፡ ይህች ዓለም የወጣቶች ብቻ ሳትሆን የሕፃናትም፣ የጎልማሶችም፣ የአረጋውያንም ዓለም ናትና ለሌላው ዕድል ስጡ፡፡ ሕይወት ረጅም መንገድ እንጂ በአንድ ትንፋሽ የምትጠናቀቅ አይደለችምና በእርጋታና በማስተዋል መጓዝን አትርሱ፡፡ ያን ጊዜ “ጐልማሶች ሆይ፥ ክፉውን ድል ነሥታችሁታልና እጽፍላችኋለሁ” የሚለው መልእክተ ጽድቅ ይደርሳችኋል፤ የድል አክሊል ይዘጋጅላችኋል፤ የመንግሥተ ሰማያት በር ክፍት ይሆንላችኋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የደረጃ ሦስት መምህራን ሥልጠና ለመጀመሪያ ጊዜ ተሠጠ

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የአቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል የደረጃ ሦስት የግቢ ጉባኤያት መምህራን ሥልጠና ለመጀመሪያ ጊዜ ከጥቅምት ፱ እስከ ፲፮ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም መስጠቱን አስታወቀ፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን አዳራሽ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ባፈራቻቸው መምህራን ለአንድ ሳምንት ሲሰጥ በቆየው ሥልጠምና ዐርባ የግቢ ጉባኤያት መምህራን የተሳተፉ ሲሆን፤  ነገረ ሃይማኖት፣ ነገረ ድኅነት፣ አንፃራዊ ትምህርተ ሃይማኖት፣ የመጻሕፍት ትርጓሜያት አጠናን ስልት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ትምህርት አበው በሃይማኖተ አበው እና አርአያነት ያለው የመምህራን ሕይወት በሚሉ ርእሶች ላይ በማተኮር ተሰጥቷቸዋል፡፡

ይህ የደረጃ ሦስት መምህራን ሥልጠና ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰጠ እንደመሆኑ መጠን የቡድን ውይይት፣ የእርስ በእርስ የልምድ ልውውጥም አድርገዋል፡፡ በተጨማሪም አገልግሎት ላይ ተሰማርተው እያገለገሉ እንደመገኘታቸው ሳምንቱን ሙሉ ምሽቱን በአገልግሎት ላይ ሰፊ ልምድ ያላቸው መምህራን እየተገኙ ልምዳቸውን አካፍለዋል፡፡

ሥልጠናውን በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የአቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል የተዘጋጀ ሲሆን፤ ደረጃ አንድ የመምህራን ሥልጠና በማእከላት፣ ደረጃ ሁለት ደግሞ በማስተባበሪያ ጽ/ቤቶች አማካይነት ይሰጣሉ፡፡ ፣ ደረጃ ሦስትን ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ በዋናው ማእከል የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ እንዲሰጥ በተወሰነው መሠረት ሥልጠናው ተካሂዷል፡፡

በዚህ ሥልጠናም ሠልጣኞች ሰፋ ያለ ትምህርት እና ልምድ መቅሰማቸውን በመግለጽ በሚሄዱበት ሁሉ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚያገለግሉ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል፡፡

ከፊት ይልቅ ትጉ (፪ኛ.ጴጥ. ፩፥፲)

በመጋቤ ሃይማኖት /  ምትኩ አበራ

ይህንን ኃይለ ቃል የተናገረው ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ነው፡፡ ኃይለ ቃሉን የምናገኘው ደግሞ በ፪ኛ ጴጥ. ፩፥፭-፲፩ ላይ ነው፡፡ ሙሉው ንባብ እንዲህ ይላል፡- “… ስለዚህ ምክንያት ትጋትን ሁሉ እያሳያችሁ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፤ በበጎነትም ዕውቀትን፤ በዕውቀትም ራስን መግዛት፤ ራስንም በመግዛት መጽናትን፤ በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰል፤ እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማችን መዋደድ፤ በወንድማማችም መዋደድ ፍቅርን ጨምሩ፤ እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ሆነው ቢበዙ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ዕውቀት ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንዳትሆኑ ያድርጉአችኋልና፡፡ እነዚህ ነገሮች የሌሉት ዕውር ነውና በቅርብ ያለውን ብቻ ያያል የቀደመውንም ኃጢአቱን መንጻት ረስቷል፡፡ ስለዚህ ወንድሞች ሆይ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ …”

ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በጥሞናና በእርጋታ ካነበብን በኋላ መልእክቱን በጥልቀት መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ርእሱን እናስተውል “ከፊት ይልቅ ትጉ” ነው የሚለው፡፡ እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ በዚህ ርእስ ሦስት ነገሮችን ብቻ እናያለን፡፡ እነርሱም፡-

፩. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባሉት እነማን ናቸው?

፪. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባልንባቸው የትጋት አቅጣጫዎች ምንድናቸው?

፫. የተባልነውን በማድረጋችን የምናገኘው ምንድነው? የሚሉት ናቸው፡፡

. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባሉት እነማን ናቸው?

ኃይለ ቃሉን በአስተውሎት ስንመለከተው ትጉ ብቻ ሳይል “ከፊት ይልቅ ትጉ” ነው የሚለው፡፡ ይህ ማለት ከትጋት በአፍአ ሆነው የሚያንቀላፉትንና በስንፍና ሰንሰለት ታስረው በተስፋ መቁረጥ ምንጣፍ የተኙትን አይመለከትም ማለት ነው፡፡ ይህ ማለት በትጋት ውስጥ ሆነው የአቅማቸውን እያከናወኑ ላሉት ትጉኀን ክርስቲያኖች የተነገረ ነው ማለት ነው፡፡ ሐዋርያው ትጋታቸውን ተቀብሎና አክብሮ ነው የሚጽፍላቸው ትጋታችሁ ጥሩ ነው፣ ግን ብቻውን በቂ አይደለም ይላቸዋል፡፡ አሁን በትጋታቸው ላይ ትጋትን እንዲጨምሩ ቀድሞ ከነበራቸው ትጋት በተጨማሪ የበለጠ እንዲተጉ ሲመክራቸው “ከፊት ይልቅ ትጉ” ይላቸዋል፡፡ ይህም ማለት ቀድሞ ይጾሙ፣ ይጸልዩ፣ ያገለግሉ ከነበረበት ትጋታቸው በተጨማሪ የበለጠ እንዲተጉ ይመክራቸዋል ማለት ነው፡፡

የተወደዳችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች እኛስ እንዴት ነን? እየጾምን ነው? በጸሎታችንስ እንዴት ነን? የማያቋርጥ የዕለት ተዕለት ጸሎት ይኖረን ይሆን? እንዲያው ለመሆኑ ከፊት ይልቅ እየተጋን ነው? ወይስ ከነአካቴው በመንፈሳዊ አገልግሎታችን ዝለናል? ምላሹ የራሳችሁ ሆኖ ለራሳችሁ ነው፡፡ ይኼኔ እኮ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከፊት ይልቅ ትጉ እያለ እንኳንስ ከፊት ይልቅ ልንተጋ መደበኛውንና የሚጠበቅብንን ክርስቲናዊ ግዴታችንን እና የአገልግሎት ድርሻችንን በአግባቡ መወጣት የተሳነን ሞልተናል፡፡ ብቻ ፈጣሪ ለሁላችንም ልቡና ይስጠን፡፡

. ከፊት ይልቅ ትጉ የተባልንባቸው የትጋት አቅጣጫዎች ምንድናቸው?

እጅግ የተወደዳችሁና የተከበራችሁ አንባብያን እስቲ አንድ ጊዜ ቀና በሉና ወደ መነሻ(መሪ) ምንባባችን ተመለሱ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በቁጥር ፲ ላይ “…መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ተጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ…” ብሎ ከመጀመሩ በፊት ከላይ እንድናነባቸውና እንድንተጋባቸው የሚያስፈልጉ ዋና ዋና ጉዳዮችን በዝርዝር አስቀምጧል፡፡ እነዚህ ጉዳዮች ስምንት ሲሆኑ፤ እነርሱም፡-

፩. እምነት                           ፭. መጽናት

፪.በጎነት                              ፮. እግዚአብሔርን መምሰል

፫. ዕውቀት                           ፯. የወንድማማች መዋደድ

፬. ራስን መግዛት                 ፰. ፍቅር ናቸው፡፡

እያንዳንዱ ክርስቲያን እነዚህን ሰፍሮና ቆጥሮ ዘወትር በሕይወቱ ውስጥ እየፈለገ ምን አለኝ? ምንስ ይቀረኛል? በማለት በትጋት እያሰላ መኖር ይገባዋል፡፡

በአርባና በሰማኒያ ቀን ከሥላሴ የጸጋ ልጅነትን ገንዘብ ያደረገ አንድ ክርስቲያን በቅድሚያ እምነት ሊኖረው ግድ ነውና ሐዋርያው በእምነት ጀመረ፡፡ እምነት ወይም ሃይማኖት ስንል ልክ እንደ አንድ ሳንቲም ሁለት አስፈላጊ ገጽታዎችን የያዘ መሆኑን ማወቅና መረዳት ያስፈልጋል፡፡ እነሱም ማመንና መታመን ይባላሉ፡፡ አንድ ክርስቲያን ሃይማኖት ወይም እምነት አለኝ ሲል በፈጣሪዬ አምናለሁ እታመንማለሁ ማለቱ ነው፡፡ ማመን ማለት ለዚህች ዓለም ሠራዒ ወመጋቢ አላት ብሎ ማመን ሲሆን መታመን ማለት ደግሞ አለ ብለን ለምናምነው አምላክ መገዛት፣ እሺ በጀ ማለት በሕጉና በትእዛዙ መጓዝ ማለት ነው፡፡ በጥቅሉ ሃማኖትና ሥነ ምግባርን ይዞ መገኘት ማለት ነው፡፡

የአንድ ክርስቲያን እምነቱ በየጊዜው ያድጋል፡፡ ይህ ማለት የማመኑና የመታመኑ ጥበብ እየተረዳው (እየገባው) ሲመጣና ራሱን ለፈጣሪና ለሕጉ ማስገዛት ሲጀምር ማመኑና መታመኑም እየጨመረ ይሄዳል ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “ስለዚህ ምክንያት ትጋትን ሁሉ እያሳያችሁ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፣ …” ብሎ ከእምነት የጀመረው፡፡ ሰው አማኝ ሆኖ የበጎነት ድርቅ ካጠቃው ደግሞ ዋጋ የለውም፡፡ አንዳንድ ሰዎች ለምሳሌ በአጽዋማት ጊዜ ውሎ ቅዳሴ እያስቀደሱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ይህ እኔ የምቆምበት ቦታዬ ነው እያሉ በቦታ የሚጣሉ ከሆነ እምነታቸው በውስጡ በጎነትና ቅንነት ይጎድለዋል ማለት ነው፡፡

አንዳንዱ ደግሞ በጎነት ይኖረውና በጎነቱ ግን ያለ ዕውቀት ሆኖ ይጎዳዋል፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ ሰዎች በበጎነታቸው ገንዘባቸውንና ዕውቀታቸውን የቤተ ክርስቲያንን እምነትና ሥርዓት ለማፍረስ ለቆሙ መናፍቃንና የውስጥ ጠላቶች ሲያውሉ ይታያል፡፡ ባለማወቅ የረዱ እየመሰላቸው ማለት ነው፡፡ በረከታቸው ይድረሰንና በአንድ ወቅት የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ “ሃይማኖት ያለ ዕውቀት ጅልነት ነው፤ ዕውቀት ያለ ሃይማኖት እብደት ነው” ይሉ ነበር፡፡ ስለዚህ ነው ሐዋርያው “በእምነታችሁ ላይ ዕውቀትን ጨምሩበት” ያለው፡፡

በዕውቀት ላይ ደግሞ ራስን መግዛት እንድንጨምር ታዘናል፡፡ ምክንያቱም በራስ መግዛት መሪ ያልተዘወረ ዕውቀት የዲያብሎስ ዕውቀት ነው፤ ያስታብያል፣ ወደ እንጦሮጦስም ያስወርዳል፡፡ በራስ መግዛት ላይ መጽናትን ጨምሩበት ካላ በኋላ እንደገና በመጽናት ላይ እግዚአብሔርን መምሰል ጨምሩበት ይለናል፡፡ አንዳንድ ሰዎች “እኔ እግዚአብሔርን ብሆን ኖሮ እንዲህና እንዲያ አደርግ ነበር” እያሉ ሲዝቱ ይስተዋላል፡፡ እግዚአብሔርን መሆን ለመፍለጥና ለመቁረጥ ወይም ለማጥፋትና ለመቅሰፍ ብቻ የሚመስላቸው ናቸው፡፡ ግን እኮ እግዚአብሔርን መሆን ውስጥ በጥፊ መመታትና መሰቀል መሸከምም አለ፡፡ ኧረ እንደውም “የማያውቁትን ያደርጋሉና ይቅር በላቸው” ማለትም አለበት፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔርን መምሰል ማለት ሆደ ሰፊ፣ ነገር አላፊ፣ ይቅር ባይ፣ ቻይና ታጋሽ መሆን ስለ ሌሎች ራስን አሳልፎ መስጠት ማለት መሆኑን ልብ ልንል ያስፈልጋል፡፡ እስኪ ቆም ብለን ራሳችንን እንመርምር፡፡

ሐዋርያው አላበቃም እግዚአብሔርን በመምሰል ላይ የወንድማማች መዋደድን ጨምሩበት ማለትም የሰፈሬ፣ የመንደሬ፣ የእናትና አባቴ … ከሚለው የወጣ የመጀመሪያውን ሰው አዳምን መሠረት ያደረገ ወንድማማችነትን ገንዘብ አድርጉ ማለቱ ነው፡፡ በዚህ የወንድማማች መዋደድ ላይ ፍቅርን ጨምሩ ይለናል፡፡ ፍቅር ምንድነው? ፍቅር እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔርን ምስክር ያደረገ ከሸፍጥና ከጨለማ ሥራ የጸዳ፣ ፍቅርን ያዙ ሲለን ነው፡፡ አንድም ፍቅር በቅዱስ ጳውሎስ አስተምህሮ (፩ኛቆሮ. ፲፫) የሚታገሰውን፣ የማይቀናውን፣ የማይመካውን፣ የማይታበየውን፣ የማይበሳጨውን፣ ከእውነት ጋር ደስ የሚለውን ቸርነት የሚያደርገውን፣ … ንጹሑን ፍቅር ገንዘብ አድርጉ ይለናል፡፡

የተወደዳችሁ አንባብያን እነዚህን ከላይ የተዘረዘሩትን ስምንቱን ዋና ዋና ቁም ነገሮች ሁል ጊዜ በሕይወታችን ውስጥ እንፈልጋቸው፤ ጨምሩ እየተባልን አንዱን ይዘን ለሌላው እንድንተጋ ታዘናል፡፡ እስኪ ቆም ብለን እናስብ፡፡ በእያንዳንዳችን ሕይወት ከስምንቱ ስንቱ አሉ? ስንቱን ይዘን ስንቱ ይቀረናል? እነዚህ የክርስትናችን ትጋት አቅጣጫዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የመንፈሳዊ አገልግሎታችን ማኅቶታት(መብራቶች) ናቸው፡፡ ስለዚህ ዘወትር በትጋት እንፈልጋቸው፡፡ አንዱን በአንዱ ላይ ለመጨመር እንትጋ ፈጣሪያችን መትጋትን ያድለን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

. የተባልነውን በማደረጋችን የምናገኘው ምንድነው?

የተወደዳችሁና የተከበራችሁ አንባብያን እንግዲህ ከላይ እንዳስቀመጥነው ስምንቱን የትጋት አቅጣጫቻዎቻችንን ተከትለን ባለን የቀድሞ ትጋታችን ላይ እነዚህን ገንዘብ ለማድረግ ዘወትር በትጋት ላይ ትጋት እያሳየን ከቀጠልን ምን እንደምናተርፍ ሐዋርያው በአጭር አገላለጥ አስቀምጦልናል፡፡ እንዲህ ሲል “እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ሆነው ቢበዙ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ዕውቀት ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንዳትሆኑ ያደርጓችኋልና”(ቁ.፰)፡፡

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱትን ስምንቱን ቁም ነገሮች እየጨመርንና እያበዛን ከሄድን ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንደማንሆን በግልጽ ቋንቋ ነግሮናል፡፡ ሥራ ፈትና ፍሬ ቢስ የሚሉት ቃላቶች ሁለት ቢሆኑም ግን አንድ ናቸው፡፡ አንዱ አንዱን ይስበዋል፤ ማለትም ሰው ሥራ ፈት ሲሆን ነው ፍሬ ቢስ የሚሆነው፡፡ ፍሬ ያለ ሥራ እንደማይገኝ ሁሉ ፍሬ ቢስነትም ያለ ሥራ ፈትነት አይኖርም፡፡

ሥራ ፈትነት በሁለቱም ዓለማት ከባድ ቢሆንም በተለይ በመንፈሳዊው ዓለም ትንሽ ለየት ይላል፡፡ “ሥራ የፈታ አእምሮ የሰይጣን ቤተ ሙከራ ይሆናል” የሚል አባባል አለ፡፡ በማቴዎስ ወንጌል ምዕ.፲፪ ላይ እርኩስ መንፈስ ከሰው እንደሚወጣ (ማውጣት እንደሚቻል) ይነግረንና በዚያው ምዕራፍ ላይ “ተመልሶ ይመጣል” ይለናል፡፡ ይህንን የሐዲስ ኪዳን መተርጉማን ሲያብራሩት ከወጣ በኋላ ተመልሶ የማደር ሥልጣን የለውም ዳሩ ግን ማሰቡ አይቀርም፡፡ ሲያስብ ግን ያ ሰው ከጾም ከጸሎት በአፉ ሆኖ ከመንፈሳዊ ሕይወቱ ከመልካም ሥራው ተዘናግቶ(ተታሎ) ቢያገኘው፡- እንዲህ ይለናል፡፡ “…ወደወጣሁበት ቤቴ እመለሳለሁ ይላል ቢመጣም ባዶ ሆኖ ተጠርጎና አጊጦ ያገኘዋል፤ ከዚያ ወዲያ ይሄድና ከእርሱ የክፉትን ሰባት ሌሎችን አጋንንት ከእርሱ ጋር ይወሰዳል፤  ገብተው በዚያ ይኖራሉ፡፡ ለዚያ ሰው ከፊተኛው ይልቅ የኋለኛው ይብስበታል …” (ማቴ.፲፪፥፵፬-፵፭)፡፡

እንግዲህ ልብ አድርጉ የሥራ ፈት አእምሮ ለሰይጣን የተጠረገና ያጌጠ ቤቱ መሆኑን እየነገረን ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሥራ ፈቶች ብዙ ይነግረናል፡፡ ሥራ ፈቶች የራሳቸውን ነፍስ ከማስኮነን አልፈው ለሌሎች ሰዎችም ጭምር አዋኪዎች ናቸው፡፡ አይሁድ እንኳን በአቅማቸው የሚፈልጉትን ተንኮል ከግብ ለማድረስ ሥራ ፈቶችን ይጠቀሙባቸው ነበር፡፡ ለምሳሌ በአንድ ወቅት ሐዋርያው ጳውሎስን በተቃወሙት ጊዜ እነዚህኑ ሥራ ፈቶች እንደተጠቀሙባቸው መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ “… አይሁድ ግን ቀንተው ከሥራ ፈቶች ክፉ ሰዎችን አመጡ፣ ሕዝቡንም ሰብሰው ከተማውን አወኩ” (ግ.ሐዋ.፲፯፥፭)፡፡

በዚህ በሥጋዊው ዓለም እንኳን ክፉ ሰዎች የክፋታቸውን ጥግ ለመግለጥና ለማሳየት በፈለጉ ጊዜ የሚጠቀሙባቸው እነዚህኑ ሥራ ፈቶችን ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓለምም ቢሆን በተቻለን መጠን ሥራ ፈት ላለመሆን መትጋት አለብን፡፡ ሥራ ማለት ከቀጣሪው አካል የምንታደለው ብቻ ግን አይደለም፡፡ ራሳችን ለራሳችን ሥራ ልንሰጠው ይገባል፡፡ ለምሳሌ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማነበብ፣ መጠየቅ፣ ለመረዳት መጣር ገዳማትንና አድባራትን እየሄዱ እጅ መንሳት፣ ማስቀደስ፣ በሰርክና በልዩ ልዩ የቤተ ክርስቲያን ታላላቅ የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብራት ላይ እየተገኙ መማር በሰንበት ት/ቤትና በመንፈሳዊ ማኅበራት ውስጥ ማገልገል … ወዘተ፡፡

የተወደዳችሁ አንባብያን ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ከላይ ያስቀመጣቸውን ስምንት ቁም ነገሮች በመሰብሰብ ከተጠመዳችሁ ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች አትሆኑም ብሎናል፡፡ ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች ካልሆንን ደግሞ የሰይጣን መፈንጫ አንሆንም ማለት ነው፡፡ እንዲህ ከሆንን ደግሞ በመጨረሻ ጊዜ በኃጥአን ሊፈርድባቸው፣ ለጻድቃን ሊፈረድላቸው የሚመጣው አምላካችን “ሑሩ እምኔየ ሳይሁን ንዑ ሀቤየ ቡሩካኑ ለአቡዬ፤ እናንት የአባቴ ቡሩካን ኑ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያዘጋጀሁላችሁን መንግሥተ ሰማያትን ውረሱ” ይለናል፡፡ ይህ እንዲሆን ግን ከፊት ይልቅ እንትጋ፡፡

ትጉኁ አምላካችን ትጋቱን ያድለን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ አሜን፡፡

በዓላማ መጽናት

በቀሲስ ዐቢይ ሙሉቀን

“ምክር ሠናይት ለኵሉ ዘይገብራ፤ ለሚያደርጋት ሁሉ ምክር መልካም ናት” በማለት ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት እንደተናገረው ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ሊቃውንት በአጠቃላይ እግዚአብሔር ድንቅ ሥራውን የሚሠራባቸው ቅዱሳን አባቶቻችን እኛ ከእግዚአብሔር ጋር ሊኖረን የሚገባው ኅብረት መሰናክል እንዳይገጥመውና በአግባቡ ጸንተን እንድንኖር ይመክሩናል። የአበው ምክር እኛ ላሰብነው ዓላማ ታማኝ እንድንሆን፣ በዚች ውጣ ውረድ በበዛባት ዓለም ስንኖር ሊደርስብን በሚችለው መከራ ሳንሸነፍ በዓላማችን ጸንተን ልንደርስበት ካሰብነው ግብ መድረስ እንዳለብን ነው።

በዓላማ መጽናት ማለት ምክንያት እየፈለጉ ያቀዱትንና ሊያከናውኑት ያሰቡትን ከመተው መቆጠብ ነው። ሰዎች በዓላማቸው ሲጸኑ ዓላማቸውን ሊያሰናክል የሚመጣባቸውን መሰናክል ሁሉ ጥበበኛው ሰሎሞን “ትዕግሥት ታላቁን ኃጢአት ያስተሠርያልና የገዢ ቁጣ የተነሣብህ እንደሆነ ሥፍራህን አትልቀቅ” በማለት እንደገለጸው በትዕግሥት ያልፉታል። (መክ. ፲፣፬) የገዢ ቁጣ ከባድ ነው፤ ይሁን እንጂ በትዕግሥት ሲያልፉት ሥርየተ ኃጢአትን፣ በክብር ላይ ክብርን፣ በጸጋ ላይ ጸጋን ያጎናጽፋልና ጥበበኛው በዓላማህ ጽና፣ ስፍራህን አትልቀቅ እያለ ይመክረናል።

ሐዋርያው ያዕቆብም “መከራን የሚታገሥ ሰው ብፁዕ ነው፤ ተፈትኖ እግዚአብሔር ለሚወዱት ተስፋ ያደረገላቸውን የሕይወት አክሊል ይቀበላልና።” በማለት በዓላማ ብንጸናና የሚመጣውን መከራ ብንታግሥ ልናገኘው የምንችለውን የሕይወት አክሊል እንደሚሰጠን ያስረዳናል። (ያዕ. ፩፥፲፪)

ከዓላማ ጽናት ጋር ተያይዞ መልካም አርአያ የሚሆኑን ታሪኮች በመጽሐፍ ቅዱስ በስፋት የተጠቀሱ ሲሆን ጥቂቶቹን እንመልከት፡-

“ጌታችን ኢየሱስም በቢታንያ በለምጻሙ በስምኦን ቤት ሳለ ዋጋው እጅግ ብዙ የሆነ ሽቱ የሞላበት የአልባስጥሮስ ብርሌ የያዘች ሴት ወደ እርሱ መጣች፤ ጌታችን ኢየሱስም በማዕድ ተቀምጦ ሳለ በራሱ ላይ አፈሰሰችው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ይህን ባዩ ጊዜ ተቆጥተው እንዲህ አሉ፡፡ ይህች ሴት ይህን ያህል ሽቱ አጠፋች ይህ በብዙ ዋጋ ተሸጦ ለድኾች ምጽዋት ይሰጥ ዘንድ ይቻል ነበርና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ዐወቀባቸውና እንዲህ አላቸው “ይህችን ሴት ለምን ታዳክሟታላችሁ ለእኔ መልካም ሥራን ሠርታልኛለችና፤ ድሆችንስ ዘወትር ታገኟቸዋላችሁ በወደዳችሁም ጊዜ በጎ ታደርጉላቸዋላችሁ፤ እኔን ግን ዘወትር የምታገኙኝ አይደለም፡፡ እርሷ ይህን በራሴ ላይ ያፈሰሰችውን ሽቱ ለቀብሬ አደረገችው፡፡ እውነት እላችኋለሁ ይህ ወንጌል በዓለሙ ሁሉ በሚሰበክበት ቦታ ይህች ሴት ያደረገችው ለእርሷ መታሰቢያ ሆኖ ይነገራል፡፡” (ማቴ.፳፮፥፮-፲፫)፤ (ማር.፲፬፥፫-፱)፤ (ዮሐ. ፲፪፥፩-፰)

ይህች ሴት ያሰበችውን ዓላማ ለማሳካት እጅግ የሚደንቅ ጽናት የሚታይባት ናት፡፡ የተጠራችው በክብር ነው “ኃጥኣንን ወደ ንስሓ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም” እንዲል። (ሉቃ. ፭፥፴፪) ስለዚህ ሰው ደግሞ በክብር ሲጠራ “ጠሪዬ አክባሪዬ” እንዲሉ አበው አክባሪዋን ሰማያዊውን ሙሽራ ሊያከብር የሚችል ዋጋው እጅግ ውድ የሆነ ሽቱ ይዛ ሄደች፡፡

ይህች ሴት ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመሄዷ በፊት ግን ዲያብሎስ ያዘጋጃቸውን መሰናከያ ፈተናዎችን አልፋለች፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ ይህች ሴት ዘማ የነበረችና ዝሙትን መተዳደሪያዋ ያደረገች ነበረች፡፡ ውበቷና ደም ግባቷ ብዙዎችን ያንበረከከ፣ ፈላጊዋ ስፍር ቁጥር የሌለው ሆኖ ሳለ ወደ ልቧ ስትመለስ ስትሠራ የነበረው ሥራ ጸያፍና በሰውም በእግዚአብሔርም ዘንድ የተጠላ እንደነ ተረዳች፡፡ የዘወትር መተዳደሪያዋን ዘግታ፤ ዳግም ወደ ዝሙት ሥራዋ ላለመመለስ የወሰነችው ውሳኔ ጽናቷን ያለመክታል፡፡ ዓላማና ፍላጎቷ ያንን የተጠላና ነውር የሆነውን ሥራ መተውና ወደ ፈጣሪዋ መመለስ ነበርና ወሰነች፡፡

ቀጥላ ያደረገችው ግን የሚገርም ነው፡፡ ስትፈጽመው የነበረው የዝሙት ሥራ ከእግዚአብሔር እንደለያት ስትረዳ በዝሙት ያጠራቀመችውን ገንዘብ ሰብስባ ውድ ሽቱ ገዝታ ለጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትቀባው ዘንድ ወደ ገበያ ወጣች፡፡ መውጣቷ መልካም ቢሆንም በመንገድ የጠበቃት ግን እጅግ ፈታኝ ባላጋራ ስለነበር በዓላማዋ ጸንታ ማለፍን ከእርሷ ይጠበቅ ነበር፡፡

ዲያብሎስ በለመደችው ወንድ መልክ ተገልጦ በመንገድ ጠብቆ ዝም ብሎ አላሳለፋትም፡፡ “እንግዳ ወንድ መጥቶብሽ ለእርሱ ልትቀቢው ሽቱ ልትገዢ ትሄጃለሽ?” አላት፡፡ እርሷም “አዎን፡፡ ከዚህ ዓለም ልዩ የሚሆን ጌታ መጥቷል” በማለት መለሰችለት፡፡ ዲያብሎስ በመልሷ እየተናደደ ሌላ ጥያቄ ደግሞ እንዲህ ሲል አቀረበላት “ፍቅሩ ያላለቀለት ወንድ መጥቶብሽ ለዚያ ልትቀቢው ሽቱ ልትገዢ ትሄጃለሽ?” አላት፡፡ እርሷም መልሳ “አዎን፡፡ ፍቅር ሰሐቦ ለወልድ ኃያል እመንበሩ ወአብጽሆ እስከ ለሞት፤ የሰው ፍቅር አገብሮት ሊሞት መጥቷል” ስትል መለሰች፡፡ ለሦስተኛ ጊዜ ተስፋ ሳይቆርጥ ”በጥቂት ገንዘብ ብዙ ገንዘብ የሚሰጥ ነጋዴ መጥቶብሽ ለእርሱ የምትቀቢው ሽቱ ልትገዢ ትሄጃለሽ?” ሲል ጠየቃት፡፡ እርሷም መልሷ “አዎን፡፡ በጥቂት ትሩፋት ብዙ ክብር የሚሰጥ ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቷልና ለእርሱ የምቀባው ሽቱ ልገዛ እሄዳለሁ” ብላ ስሙን ስትጠራበት እንደ ትቢያ በኖ፣ እንደ ጢስ ተኖ ጠፍቶላታል፡፡

ዲያብሎስ ከአንድም ሦስት ጊዜ ሊያሰናክላት ጥረት አድርጓል፡፡ ነገር ግን ዓላማዋ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ማግኘት፣ በፊቱም መንበርከክና ስለ ኃጢአቷ እያለቀሰች ሽቱውን ትቀባው ዘንድ ነውና ዲያብሎስ ያቀረበላትን የማሰናከያ መንገዶችን ሁሉ በዓላማዋ በመጽናት በአምላኳ በጌታዋ ስም ድል ነሳችው፡፡

ስጦታውንም ስንመለከት ውድ የሚያደርገው ከእሷ ጥረትና ቅንነት አንጻር እንጂ ለጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህ የሚመጥን ሆኖ አይደለም፡፡ ዙፋኑ እንኳ በሰማያውያን ሱራፌል በሰማያዊው ማዕጠንት የሚታጠን ጌታ ምድራዊ ሽቱ እንዴት ሊመጥነው ይችላል? ሊሆንም አይችልም፡፡ ሃያ አራት ሰዓት ሙሉ ከምስጋና የማይለዩ ንጹሐን፣ ቅዱሳን፣ ትጉኃንና ሰማያውያን መላእክት በሚያቀርቡት ሰማያዊ ሽቱ የሚታጠን አምላክ ዕድሜ ዘመኗን በሙሉ በዝሙት የኖረች ሴት በምታቀርበው ሽቱ ለዚያውም በዝሙት በተሰበሰበ ብር በተገዛ ሽቱ እንዴት ሊወሰን ይችላል?  ግን እሷ መሐሪነቱን ተረድታለች፤ የኃጢአተኛን መመለሱን እንጂ ሞቱን የማይሻ ቸርና ይቅር ባይ አምላክ እንደሆነ ዐውቃለች፤ የዛሬ መመለሷን እንጂ የትናንትና ማንነቷን እየተመለከተ እሷን የማያሸማቅቅ ይልቁንም ቸር አባት እንደሆነ አምናለች ፡፡ ስለዚህ አደረገችው፤ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የአመጣችለትን ሽቱ ደስ ብሎት ተቀበላት፡፡

እጅግ የሚገርመው ግን እሷ ያልተቆጨችበትን ውድ ሽቱ ተመልካቾችን አላስደሰታቸውም ነበር፡፡ ይህ እኮ ተሸጦ ለድኾች ቢሰጥ ይቻል ነበር በማለት አጉል ተቆርቋሪ መሰሉ፡፡ ግን ለምን ተቃወሟት የሚለውን በተወሰነ መንገድ ማየቱ የተሻለ ነው፡፡ ከተቃዋሚዎች አንዱና ዋነኛው ይሁዳ ነበር፡፡ ይሁዳ ደግሞ በዚያን ሰዓት ገንዘብ ቤት ነበርና ወደ ከረጢቱ ከሚገባው ሁሉ ከዐሥር አንድ ይደርሰው ነበር፡፡ ሽቶው የተገዛበት ዋጋ ሦስት መቶ ወቄት ወርቅ ነው፡፡ ስለዚህ ሠላሳ ወቄት ወርቅ ይደርሰው ነበር ግን ስጦታው በብር ሳይሆን በዓይነት ስለቀረበ ያን ድርሻ ማግኘት አልቻለም፡፡ በዚህ ምክንያት ለድኾች ያዘነ በመምሰል ለሱ የቀረበትን ድርሻ እያሰላሰለ ተቃውሞውን አቅርቧል፡፡

ጊዜው መልካም ነገር የሚደረግበት፣ ሰዎች ከኃጢአት ወደ ሥርየት የሚመለሱበት፣ ለበጎ ሥራ የሚነሳሱበት ነበር፡፡ በአንጻሩ ደግሞ መንፈሳዊውን ቅናት የሚያደበዝዝና ተስፋ የሚያስቆርጥ፣ ተቃውሞ የበዛበትና ሰይጣናዊው ቅናት የሰፈነበትም ነበር፡፡ በመሆኑም እግዚአብሔር የፈቀደላቸው ያላቸውን ሁሉ የሚሰጡበት፣ ለገንዘባቸው ቀርቶ ለሰውነታቸው የማይሳሱበት፣ በአንጻሩ ደግሞ ሰዎች ስለ ሰጡ የሚናደዱበት “ነጋዴ አያዝንም እሱ ስለ ከሰረ ወንድሙ እንጂ ስለ ቀረ” እንዲሉ ይህ ዓይነት ከንቱ ምኞት የሰፈነበት ነበርና በጎ በሚያደርጉት ላይ ተቃዋሚዎች በዝተው ነበር፡፡ መድኅን ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ሁሉን አዋቂ ነው ምን ለምን እንደሚሆን ያውቃልና በመሆኑም አክብሮ ተቀበላት። ነገር ግን ሰዎች ሲቃወሙ እሱ እንዲህ አክብሮ የተቀበለበት ምክንያት ምን ይሆን ስንል የሚከተሉትን ምክንያቶች ማየት ይቻላል፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ እርሱ የሚገኘው በዚያ ዕለት ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ “ድሆችንስ ዘወትር ታገኟቸዋላችሁ በወደዳችሁም ጊዜ በጎ ታደርጉላቸዋላችሁ እኔን ግን ዘወትር የምታገኙኝ አይደለም፡፡” በማለት እንደተናገረው በአካለ ሥጋ ሆኖ ሽቱ የሚረበረብለት የሚጨበጥ የሚዳሰስ ሆኖ የምታገኝበት ጊዜ ያን ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እዚህ ላይ ጥንቃቄ ማድረግ ያለብን ከዚያ በኋላ ከሥጋው ይለያል ማለት አይደለም፡፡ በአይሁድ እጅ ተይዞ ወደ ፍርድ የሚቀርብበት፣ ወደ መስቀል የሚወጣበት ጊዜ እንደ ደረሰና እሷ የማታገኝበት ቀን እንደሚመጣ ለማመልከት ነው፡፡

በሁለተኛ ደረጃ እሷ ወጣኒ ናትና እንዳትሰናከል ነው፡፡ በጀማሪነት ደረጃ ያለን ሰው የሚያስተምሩትን ሊመጥኑለት፣ ምን ማድረግ እንደሚገባ የቅደም ተከተል ጉዳይ ላይ ማተኮር እንደሚገባ፣ ቀስ እያለ ወደ ምን መሄድ እንዳለበት ሲያስተምር ነው፡፡ ምክንያቱም ክርስትና ቀስ በቀስ የሚለማመዱት ሕይወት ነውና፡፡ ብርሃነ ዓለም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ወንድሞቼ ሆይ እኔስ የሥጋና የደም እንደ መሆናችሁ ክርስቶስንም በማመን ሕፃናት እንደ መሆናችሁ እንጂ እንደ መንፈሳውያን ላስተምራችሁ አልቻልሁም፤ ወተትን ጋትኋችሁ ጽኑዕ መብልም ያበላኋችሁ አይደለም፤ ገና አልጠነከራችሁና፡፡” (፩ቆሮ ፫፥፩-፪) በማለት እንዳስተማረን በጀማሪነት ያለን ሰው በለመደው፣ በሚችለውና በሚወደው ነገር መሳብ ተገቢ ስለሆነ ሰማያዊው ሙሽራ ኢየሱስ ክርስቶስም የአመጣችውን ስጦታ በደስታና በአክብሮት ተቀበላት፡፡

በሦስተኛ ደረጃ አንድ ሰው ቀድሞ ምን ማድረግ እንዳለበት የሚያማክር ከሆነ እዲህ አድርግ ሊሉት ይገባል ከሆነ በኋላ ግን እንዲህ ማለት ያሰናክላልና ተዉዋት አላቸው፡፡ ተዉዋት ብቻም አይደል ያላቸው ለምን ታሰናክሏታላችሁ ነበር ያላቸው፡፡ ይህም ማለት በትርጓሜ ወንጌል እንደተጻፈው አንድ ሰው ምጽዋት መስጠት ቢፈልግና ለቤተ ክርስቲያን ልስጥ ወይስ ለነዳያን ልስጥ ብሎ ቢያማክር ሕንፃ እግዚአብሔር የሆነው የሰው ልጅ በርኀብ በጥም እየተሠቃየ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያንን ገንባ ከማለት ቅድሚያ ለሰው ልጅ መስጠት እንዳለበት ማስገንዘብ ይገባል፡፡ ሰውየው በራሱ ተነሳሽነት ካደረገው በኋላ ግን እንዲህ ማድረግ አልነበረብህም ቢሉት ጭራሽ በጎ ሥራ በመሥራቱም ተጸጽቶ ለወደፊቱም መልካም ነገርን ከማድረግ ሊቆጠብ ስለሚችል የሠራውን መልካም ሥራ ጥሩ እንዳደረገ ማበረታታት ይገባል፡፡ እንግዲህ ይህን ሁሉ ምሥጢር የሚያውቀው ማዕምረ ኅቡአት ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣለትን ክቡር ስጦታ አክብሮ ተቀብሏል፡፡

ከማርያም እንተ እፍረት የምንማራቸው በርካታ ቁም ነገሮች አሉን፡፡ እነርሱም፡- ለበጎ ነገር መሽቀዳደምን፣ የዓላማ ጽናትን ይልቁንም ለንስሓ መዘናጋት እንደሌለብን መረዳት እንችላለን፡፡ ትርጓሜ ወንጌል እንደሚነግረን ማርያም እንተ እፍረት ይህ ቀረሽ የማትባል መልከ መልካም ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን መላ ሰውነቷን በሚያሳይ በቁም መስተዋት ራሷን እየተመለከተች ግን ያን የሚመስል ውበት እንደሚያልፍ እንደሚረግፍ ተረዳች፡፡ ለዚህ መድኃኒቱ ደግሞ ንስሓ መግባት እንደ ሆነ ተረዳችና ዘመኗን ሙሉ በዝሙት የአጠራቀመችውን ገንዘብ በመያዝ ሥርየትን ለሚያድለው፣ ኃጢአትህ/ሽ ተሰርዮልሃል/ሻል ለሚለው ሊቀ ካህናት መድኅን ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ የሚገባውን ሽቱ ገዝታ ወደ እሱ ሄደችና ማድረግ የሚገባትን አደረገች፡፡

ማርያም እንተ እፍረት ወደ ልቧ በተመለሰች ጊዜ ሳትውል ሳታድር ፈጥና ነው ንስሓን ወደሚቀበለው ሊቀ ካህናት የሄደችው፡፡ ይህ ብቻ አይደለም በመንገድ ላይ የዲያብሎስን ፈተና በድል ብትወጣውም ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደረሰችም በኋላ በደቀ መዛሙርቱ በተለም በአስቆርቱ ይሁዳ መሰናክሎች ገጥመዋታል፡፡

ከደቀ መዘሙርቱ መካከል አዛኝ ለድሆች በጎ አሳቢ በመምሰል ይህ ተሸጦ ለድሆች ሊሰጥ በተገባ ነበር በማለት ያደረገችውን ሥራ እንደ ጥፋት ቆጥረውት ነበር፡፡ ነገር ግን በፈጣሪዋ ፊት ተንበርክካለችና የዓላማዋን ጽናት፣ የልቧን መሻት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አውቋልና እርሷ ሳትሆን ስለ እርሷ ክርስቶስ “መልካም አደረገች ለምን ታሰናክሏታላችሁ” በማለት ሥራዋን አደነቀላት፡፡ እንዲያውም ይህ የእሷ ሥራ በአራቱም ወንጌላውያን ሲነገር እንደሚኖር በመግለጽ አስረዳቸው፡፡ ማሰናከያዎቹንም ሁሉ አስወገደላት፡፡

ስለዚህ እኛም ወደ መልካም ነገር ስንሄድ በየመንገዱ እየጠበቀ ለዚያውም በምናውቀውና በምንወደው አካል ዲያብሎስ እያደረ እንዳያሰናክለን ትጥቃችንን ልናጠብቅ፣ በዓላማችንም ልንጸና ይገባል፡፡

በተጨማሪም በመጽሐፍ ቅዱስ በዓላማቸው ጸንተው በእግዚአብሔር የተመሰከረላቸው፣ በክብር ላይ ክብር የታደላቸው፣ በርካታ ሰዎችን መጥቀስ ይቻላል።

ዮሴፍ በምድረ ግብፅ ያውም በስደት ላይ ሳለ በዓላማው በመጽናቱና በወጣትነት ዘመን እያለ እንኳን የወጣትነት ስሜት ሳያሸንፈው በፈርዖን ሚስት የቀረበለትን የዝሙት ጥያቄ ሳያመነታ በድል ተወጥቶታል፤ በንጉሡ ፈርዖን ዘንድም እንዲከበር፣ ቤተሰቦቹን ከነበረው ረኀብ እንዲታደግ ዛሬም ሕያውና ዘለዓለማዊ ስም ከፈጣሪው ዘንድ ተሰጥቶት በመልካም አርዓያነቱ ስንጠራው እንኖራለን። ይህ ማለት ግን መከራውን በትዕግሥት አልፎት እንጂ ምንም ዓይነት ፈተና ሳይገጥመው ስለ ኖረ አልነበረም።

ሌላው በዓላማ ስለ መጽናት ከሚያስገነዝቡን ታሪኮች መካከል የፃድቁ የኢዮብ ሕይወት ነው፡፡ ዲያብሎስ ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅር አስጥሎ ልጆቹን በሞት፣ ሀብት ንብረቱን በማውደም፣ እርሱንም ከራስ ጠጉሩ እስከ እግር ጥፍሩ በደዌ ቢመታም፤ ሚስቱንና ወዳጆቹን ቢያስነሳበትም እግዚአብሔርን ረግሞ እንዲሞት ቢገፋፉትም በዓላማው በመጽናት “እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔር ነሣ፤ የእግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን” በማለት ከዲያብሎስ ወጥመድ አምልጧል፡፡

ከላይ የተጠቀሱት ባለ ታሪኮችና ታሪካቸውን ጠቀስን እንጂ ጌታችን መድኀኒታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም  ወደዚህ ምድር የመጣበት ዋናው ዓላማ የሰውን ልጅ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመመስና የገባውን ቃል ለመፈጸም ሲሆን በሥጋው በዲያብሎስ ተፈትኗል፡፡ ዲያብሎስ ሦስት ዋና ዋና ፈተናዎችንም አቅርቦለታል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድረ በዳ ሄዶ ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ጾመና ከጸለየ በኋላ ተራበ፡፡ የሚፈታተነውም ዲያብሎስ ቀርቦ “አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህስ እነዚህን ድንጋዮች ዳቦ እንዲሆኑ እዘዝ” አለው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ ሰው የሚኖረው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣው ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ እንዳይደለ ተጽፏል፡፡” በማለት ድል ነስቶታል፡፡ ነገር ግን ዲያብሎስ ስልቱን በመቀየር በሌላ ፈተና ደግሞ መጣበት፡፡ ወደ ቅድስት ከተማ ወስዶ በቤተ መቅደሱ ጫፍ ላይ አቁሞት “አንተ በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህስ ከዚህ መር ብለህ ወደ ታች ውረድ ይጠብቁህ ዘንድ ስለ አንተ መላእክቱን ያዝዝልሃል፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰነካከል በእጃቸው ያነሱሃል ተብሎ ተጽፏልና” አለው፡፡ ጌታችንም “አምላክህ እግዚአብሔርን አትፈታተነው ተብሎ ደግሞ ተጽፏል” ሲል ድል ነሣው፡፡ ዲያብሎስ ለሦስተኛ ጊዜ እጅግ ረጅም ወደ ሆነ ተራራ አውጥቶት “የዓለሙን ሁሉ መንግሥታት ክብራቸውንም ሁሉ አሳየው፡፡ ብትሰግድልኝ እጅ ብትነሳኝም ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ “አንተ ሰይጣን ከአጠገቤ ሂድ ለጌታህ ለእግዚአብሔር ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ ተብሎ ተጽፋል” አለው፡፡ ከዚህም በኋላ ዲያብሎስ ተወው እነሆም መላእክት ሊያገለግሉት መጡ ይለናል መጽሐፍ ቅዱስ፡፡ (ማቴ.፬፥፩-፲፩)፡፡

ዛሬም እኛ በእግዚአብሔር ቸርነት ፈተናውን ሁሉ እናልፋለን እንጂ ሰው በራሱ ምንም ማድረግ እንደማይችል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ በመዋዕለ ሥጋዌው ሳለ “እኔ የወይን ግንድ ነኝ፤ ቅርንጫፎቹም እናንተ ናችሁ፤ በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ ብዙ ፍሬ የሚያፈራ እርሱ ነው፤ ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና” ብሎ እንዳስተማረን ፈተናውን ያርቅልን ዘንድ እየተማጸንን በሥራም እየገለጥን እርሱን መስለን ልንኖር ይገባናል፡፡ እንደ ቃሉ ተመላልሰን፣ የሚፈታተነን ዲያብሎስ በመንፈሳዊ ጦር ማለትም በጾም፣ በጸሎት እና በስግደት እንዲሁም መንፈሳዊ ትሩፋትን በመሥራት ንስሓ ገብተን እግዚአብሔር አምላካችንም ንስሓችንን ተቀብሎ መሰናክሎችን ሁሉ የምናልፍበትን ኃይል እንደሚሰጠን አምነን እስከ መጨረሻው በዓላማችን ጸንተን መንግሥቱን እንወርስ ዘንድ መበርታት ይገባናል፡፡ ለዚህም የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዳሳን ቃል ኪዳንና በረከት አይለየን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር