መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!

በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት እንዲሁም ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፡- እግዚአብሔር አምላካችን በይቅርታውና በምሕረቱ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ አምስት ዓመተ ምሕረት የድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ።

ወእምኵሉሰ ዘይቀድም ተፋቀሩ በበይናቲክሙ በምልአ ልብክሙ እስመ ተፋቅሮ ይደፍኖን ወይደመስሶን ለኵሎን ኃጣውእ፤ ከሁሉ አስቀድሞ በሙሉ ልባችሁ እርስ በርሳችሁ ተፋቀሩ፣ መፋቀር ሁሉንም ዓይነተ ኃጢአት ይሸፍናልና ይደመስሳልምና” (፩ጴጥ. )

ሁላችንም እንደምናውቀው የቅዱስ ወንጌል አስተምህሮ መሠረትና ጣርያ ወለልና ግድግዳ በፍቅርና በፍቅር ብቻ የተገነባ ነው፤ ፍቅር እግዚአብሔር ዓለምን ያዳነበት መድኃኒት ነው፣ ፍቅር የጥላቻና የመለያየት ግንብን ንዶ ይቅርታንና አንድነትን የሚገነባ ጠንካራ ዓለት ነው፤ ፍቅር መጽናናትንና ደስታን የሚያፈራ ጣፋጭ ተክል ነው፤ በፍቅር ለፍቅር የሚደረግ ሁሉ ፍሥሐን እንጂ ጸጸትን አያስከትልም፤ በመሆኑም በሰብኣዊ ድክመት ምክንያት ሰዎች ፍቅርን ሙሉ በሙሉ በሚፈለገው ደረጃ ባንጠብቀውም በዓለማዊም ሆነ በመፈንሳዊ ሕይወት ከፍቅር የበለጠ ጠቃሚ ነገር የለም፤ ፍቅር የማይሻርና ለዘላለሙ ጸንቶ የሚኖር እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ተመዝግቦአል፤ ምክንያቱም ፍቅር ከሞት ቡኋላም ቢሆን በእግዚአብሔር መንግሥት ይቀጥላልና ነው፤ ዛሬ የሚጀመረው የድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታም በፍቅር ለፍቅር የተፈጸመ ነው፣ ይኸውም ቅዱሳን ሐዋርያት የድንግል ማርያምን የማረፊያ ቦታ ለማየት ሲሉ የጾሙት ጾም ነው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት የገለፁት ፍቅረ ድንግል ማርያምን ብቻ ሳይሆን ያረፈችበትንም ቦታ ጭምር ያመለከተ ነበረ፥ ይህ ሊሆን የቻለው ከልብ የሆነ እውነተኛ ፍቅር በሐዋርያት ዘንድ ስለነበረ ነው፡፡

እኛም ዛሬ የምንጾመው ይህንን የማርያም ጾም እንደ አበው ሐዋርያት ፍቅረ ድንግል ማርያም በልባችን ውስጥ ተተክሎ ስላለ ነው፤ እግዚአብሔር በፍቅርና በሃይማኖት የሚቀርብለትን ሁሉ ይቀበላልና የሐዋርያትን ጾምና ጸሎት ተቀብሎ ጥያቄአቸውን መልሶአል፡፡ ዛሬም ይህንን ጾም የምንጾመው እግዚአብሔር ጾማችንን ተቀብሎ የልባችንን መሻት ይፈጽምልናል ብለን ነው፣ በፍቅርና በሃይማኖት እስከ ጾምን ደግሞ እግዚአብሔር ይቀበለናል። 

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

እንደ እግዚአብሔር ቃልም እንደ አባቶቻችን ትውፊትም የጾመ ፍልሰታ ጾም ሲጾም የበደለ ይቅርታ ጠይቆ፤ ተገቢውንም ካሣ ከፍሎ፣ ቂም በቀሉን አሰርዞ፣ ፍቅርን መሥርቶ ነበረ፤ የተበደለም በበኩሉ ዕርቅን አውርዶ፣ ይቅርታን ሰጥቶ የአእምሮ ማለስለሻና ማስረሻ የሆነውን ካሣውን ተቀብሎ ቂሙንና በቀሉን ከአእምሮው አውጥቶና አጽድቶ፣ ለእግዚአብሔር ስል ከልቤ ይቅር ብያለሁ ብሎ፤ ስመ እግዚአብሔርን ጠርቶ በፍቅር ይታረቃል፡፡

በዚህ ሁኔታ ፍጹምና ልባዊ ፍቅር ተይዞ ሲጾም ሁሉም ዓይነት ኃጢአት ሙሉ በሙሉ ይደመሰስለታል። እግዚአብሔርም ይቅርታ ጠያቂውንም፣ ይቅርታ ሰጪውንም አሸማጋዩንም ይባርካል ።ማኅበረ ሰቡም በዚህ ቅዱስና ሃይማኖታዊ ባህልና ትውፊት ተጠብቆ ለብዙ ዘመናት አንድነቱንና ሃይማኖቱን ወንድማማችነቱንና ነጻነቱን አስጠብቆ እስከ ዛሬ ደርሶአል፤ ይህ ለሀገራችን ታላቅ የሆነ የእግዚአብሔር በረከት ነበረ፤ ይህ እውነተኛ በረከት በአሁኑ ጊዜ ቸል በመባሉ ፈተናችን በዝቶአል፤ እንደ እውነቱ ከሆነ ሰው በኃጢአት ከወደቀበት ጊዜ ጀምሮ ጥልና መገዳደል በየትኛውም ጊዜ፣ በየትኛውም ሀገር በየትኛውም ማኅበረ ሰብ ይከሠታል፣ ዛሬም በሀገራችን በተፈጠረው አለመግባባት ከባድ ችግር ተፈጥሮአል፣ የሚያስገርመው ነገር ቢኖር እንዴት እንደ ባህላችንና እምነታችን በቀላሉ በዕርቅና በይቅርታ ማስተካከል አቃተን የሚለው ነው፤ የዘመናችን ልዩ ነገር ይህ ነው፤ ለዚህም ብዙ የተለያየ ምክንያት ሊኖረው ይችላል፤ በሃይማኖት ዓይን ሲታይ ግን ለእግዚአብሔር ቃል የምንሰጠው ክብር በእጅጉ ስለተቀነሰ ነው የሚል ሆኖ ይገኛል፤ ይህ ዝንባሌ አሁን ላለውም ሆነ ለሚመጣው ትውልድ አደገኛ ስለሆነ የኦርቶዶክስ ሕዝበ ክርስቲያንም ሆነ ሌሎቹ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ይህንን በጥልቀት ሊያጤኑትና ሊያርሙት ይገባል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናንት!

ሽማግሌ የሀገር በረከት ነው፤ አስታራቂ ሽማግሌ የችግር ሐኪምና ፈዋሽ ነው፤ የፍቅርና የተግባቦት መሐንዲስም ነው፤ በእግዚአብሔርም “የሚያስታርቁ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው” ተብሎ ውዳሴ ተችሮአቸዋል፣ እነዚህን ሽማግሌዎች ተጠቅመን ችግሮቻችንን መፍታት ጊዜው የሚጠይቀው አስገዳጅ ጉዳይ ሆኖአል፤ ሁሉም ታየ፤ ሁሉም ተሞከረ፤ ዘላቂ መፍትሔ ሲያመጣ ግን አልታየም፤ እንዲያውም ችግሩ ወደ ሃይማኖት ተዛምቶ ቤተ ክርስቲያንም የገፈቱ ቀማሽ ለመሆን ተገዳለች፡፡

በተጨባጭ እንደሚታወቀው ሕዝብንና ሃይማኖትን ነጣጥሎ ሰላምን ማረጋጋጥ ከቶውኑ ሊታሰብ አይችልም፤ ምክንያቱም ሕዝብ የሃይማኖቱ ቤተሰብ ነው፣ ሃይማኖቱም በሕዝቡ መንፈስ ውስጥ ነግሦ የሚኖር መለኮታዊ ኃይል ነውና፣ ከዚህ አንጻር “ወልድ ሲነካ አብ ይነካ እንደሚባለው ሕዝቡ ሲነካ ሃይማኖቱ ይነካል፤ ሃይማኖቱ ሲነካ ደግሞ ሕዝቡ ይነካል፤ በመሆኑም በተካሄደው ግጭት ብዙ ነገሮች መመሳቀላቸው የማይካድ ቢሆንም ችግሩ በዕርቅና በካሣ በይቅርታና በመተው ካልተዘጋ ለማንም ስለማይበጅ ከባድ ጉዳት የደረሰባቸው ወገኖች ለዕርቅ ዝግጁ እንዲሆኑ፣ የበደሉም እንዲክሱ የሀገር ሽማግሌዎችም የማስታረቅ ሥራን በሐቅ በገለልተኝነትና ዕንባን በሚያደርቅ ስልት እንዲሸመግሉ መንግሥትም የበኩሉን ድጋፍ እንዲያደርግ በዚህ አጋጣሚ በእግዚአብሔር ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም

የገጠመንን ፈተና ሁሉ ሊያቀልልንና ሊያስወግድልን የሚችል እግዚአብሔር ስለሆነ በዚህ የጾመ ማርያም ወቅት ምእመናን በተመሥጦና በንሥሐ ሕይወት ለእግዚአብሔር በመንበርከክ ስለ ሰላምና ፍቅር እንዲማፀኑ፣ ካላቸውም በረከት ለተራቡትና ለተፈናቀሉት እንዲለግሱ ሁሉም ወገኖች በሆነው ነገር ይብቃን ብለው ወደ ሰላማዊ አማራጭ እንዲቀርቡ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

መልካም የጾመ ማርያም ሱባዔ ያድርግልን

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

 ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ነሐሴ 2015 ..

ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር

ክፍል ሁለት

በእንዳለ ደምስስ

“ግቢ ጉባኤ ባይኖርና ወደ ቤተ ክርስቲያን ባንመላለስ በዓለም ጠፍተን እንቀር ነበር”

(ዶ/ር ምንተስኖት መንግሥቱ)

የተከበራችሁ የማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ድረ ገጽ ተከታታዮች፡- “ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር” በሚል ርእስ በክፍል አንድ ዝግጅታችን ከቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤያት ከዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ ተመራቂዎች 3.99 ከፍተኛ ነጥብ በማምጣት የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ከሆነችው እኅታችን ውብነሽ ለማ ጋር ያደረግነውን አጭር ቆይታ አቅርበንላችኋል፡፡ በክፍል ሁለት ዝግጅታችን ደግሞ ከሌሎች ተመራቂዎች ጋር የምናደርገውን ቆይታ ትከታተሉ ዘንድ እነሆ፡-

ዶ/ር ምንተስኖት መንግሥቱ በ፳፻፲፭ ዓ.ም ከጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ትምህርት ክፍል በእንስሳት ሕክምና ትምህርቱን አጠናቋል፡፡ በሦስት ነጥብ ዘጠኝ ስምንት (3.98) አጠቃላይ ውጤት ዩኒቨርሲቲው ያዘጋጀውን ዋንጫና ሜዳሊያ ተሸላሚ ለመሆን በቅቷል፡፡ በዩኒቨርሲቲው እና ስለ ግቢ ጉባኤ ቆይታው ጠይቀነዋል፡-

ዶ/ር ምንተስኖት እንዲህ ይገልጸዋል፡- “በዩኒቨርስቲ ቆይታዬ የምችለውን ያህል ጥረት ማድረጌ እንዳለ ሆኖ የእግዚአብሔር እገዛና ቸርነት አልተለየኝም፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ሳለሁም በቅድመ ግቢ ጉባኤ እሳተፍ ስለነበር ዩኒቨርሲቲ ስገባ ቀጥታ ያመራሁት ወደ ግቢ ጉባኤ ነው፡፡ እንዲያውም እኔና ጓደኞቼ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ስንሄድ በአባቶች ቡራኬ ነበር የተሸኘነው፡፡ በተጨማሪም በቅድመ ግቢ ጉባኤ ውስጥ ከእኛ ቀድመው ዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ወንድሞችና እኅቶች ተጋብዘው ተሞክሯቸውን ያካፍሉን ነበር፡፡ ወንደሞችና እኅቶችም በጥሩ ሁኔታ ነው የተቀበሉኝ፡፡ በዙሪያዬም መልካም ኦርቶዶክሳውያን ቤተሰቦችና ዩኒቨርሲቲ ስገባም ያጋጠሙኝ ጓደኞቼ ለቤተ ክርስቲያንና ለትምህርታቸው ትኩረት የሚሰጡ ስለነበሩ ለውጤታማነቴ አስተዋጽኦ አድርገዋል ማለት እችላለሁ፡፡ በቆይታዬም ለትምህርቴና ለቤተ ክርስቲያን ቅድሚያ በመስጠቴ ለውጤት በቅቻለሁ” ሲል ይገልጻል፡፡

ጓደኛን በተመለከተም “በዩኒቨርሲቲ ቆይታችን ውስጥ ጓደኛ ትልቁን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ተመሳሳይ ዓላማ ከሌላቸው ተማሪዎች ራስን ማራቅም ይገባል፡፡ ወደ ዩኒቨርሲቲ ስሄድ ዓላማዬ መማር ነው፡፡ መማር ብቻም ሳይሆን ወደፊት ለሚኖረኝ ሕይወት መሠረት የምጥልበት ስለሆነ ከሌሎች የተሻለ ሆኜ ለመገኘት መሥራት እንዳለብኝ ራሴን አሳምኜ ነው የገባሁት፡፡ ስለዚህ ከማይመቹ እና የሕይወት አቅጣጫዬን ከሚያስቱ ተማሪዎች መራቅ ነበረብኝ፤ ይህንንም አድርጌዋለሁ፡፡ ጓደኞቼ ጥሩዎች ስለነበሩ ጅግጅጋ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን እንሄዳለን፤ መርሐ ግብሮች አያመልጡንም፣ ቅዳሜና እሑድ ደግሞ በግቢ ጉባኤያችን የተዘጋጀውን ጉባኤ እና ተከታታይ ትምህርት እንሳተፋለን፤ ቀሪውን ጊዜ ደግሞ ለትምህርት እናውለዋለን፡፡ በቃ የእኔ ሕይወት በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ይህ ነበር ማለት እችላለሁ” በማለት ቆይታውን ይገልጻል፡፡

ከጊዜ ጋር የነበረውን አጠቃቀምም በተመለከተ “አንድም ደቂቃ ትሁን ዋጋ አላት” ይላል ዶ/ር ምንተስኖት፡፡ አያይዞም “የገባሁበት ትምህርት ክፍል ከፍተኛ ንባብ የሚጠይቅ ክፍል ነው፡፡ ስለዚህ አብዛኛውን ጊዜዬን የማሳልፈው በማንበብ ነው፡፡ ይህንንም በእቅድ መምራት ያስፈልጋል፡፡ አንድ ጊዜ ካቀድከው እቅድ ከተደናቀፍህ ወደ ትክክለኛው አቅጣጫ ለመምጣት ያስቸግራልና ከፍተኛ ጥንቃቄ አደርግ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ውጤታማ መሆን የቻልኩት” በማለት ተሞክሮውን አጋርቶናል፡፡

ግቢ ጉባኤን በተመለከተ ሲገልጽም “በግቢ ጉባኤ ውስጥ መቆየቴ አንዱ የውጤታማነቴ ምሥጢር ነው፡፡ በግቢ ጉባኤ ያገኘሁት ትምህርት በመንፈሳዊ ሕይወቴም ብቻ ሳይሆን ዓለም ውጣ እንዳታስቀረኝ ትልቅ ትጥቅ ሆኖኛል፡፡ የሚገጥሙኝን ፈተናዎች ለመወጣትና ራሴም በትክክለኛው መንገድ መራመድ እንድችል ትልቅ አቅም ፈጥሮልኛል፡፡ ግቢ ጉባኤ ባይኖርና ወደ ቤተ ክርስቲያን ባንመላለስ ኖሮ በዓለም ጠፍተን እንቀር ነበር፡፡ በግቢ ጉባኤ መታቀፋችን ዋጋው ብዙ ነው” ብሏል፡፡

በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ለሚገኙ ወንድሞችና እኅቶች ባስተላለፈው መልእክትም “ዋናው ዩኒቨርሲቲ ገብቻለሁ ማለት ሳይሆን ለትምህርታቸው ልዩ ትኩረት መስጠት አለባቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውም እየበረቱ እግዚአብሔር እንዲያግዛቸው ራሳቸውን ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጋር ማቆራኘት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ነገ ነገ እያሉ መዘናጋት ብዙ ዋጋ ስለሚያስከፍል የውሳኔ ሰው መሆን፣ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ያለው ሕይወት ለውጤት እንደማያበቃ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ፈተና ቢገጥም እንኳን እግዚአብሔር ፈተናውን አሳልፎ እንደሚያሻግር መረዳት መልካም ነው፡፡ ይህን ካደረግን እግዚአብሔር አብዝቶ ይባርከናል” ሲል ምክሩን ለግሷል፡፡

የተከበራችሁ የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ድረ ገጽ ተከታታዮች በክፍል ሦስት ዝግጅታችን ደግሞ ከሌሎች ውጤታማ ተመራቂዎች ጋር ያደረግነውን ቆይታ ይዘን እንቀርባለን፡፡ ይቆየን፡፡

ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር

ክፍል አንድ

በእንዳለ ደምስስ

ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ካለፉት ሠላሳ አንድ ዓመታት ጀምሮ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ በተሰጠው ኃላፊነት መሠረት በሀገር ውስጥ እና በውጪ ሀገራት የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በማስተማርና በማስመረቅ የድርሻውን በመወጣት ላይ ይገኛል፡፡ ወደፊትም ይህንን ኃላፊነቱን ለመወጣት ዘመኑ የዋጀ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቶችን በመስጠት ተመራቂዎች ሀገራቸውንና ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ እንዲሆኑ በትጋት ይሠራል፡፡ በየዓመቱም በርካቶች በተማሩት ትምህርት ውጤታማ ሆነው ዋንጫና ሜዳልያ ተሻላሚዎች ሆነዋል፡፡ “ለዚህ ውጤት እንድንበቃ ማኅበረ ቅዱሳን ትልቁን ድርሻ ይወስዳል” በማለት ዋንጫና ሜዳልያቸውንም ለማኅበሩ ሲያበረክቱ መመልከት የተለመደ ሆኗል፡፡

በ፳፻፲፭ ዓ.ም የቤተ ክርስቲያንና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርታቸውን አጠናቀው ከተመረቁት ውስጥ በርካቶች የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚዎች ሆነዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን ስለ ቆይታቸውና ስለ ውጤታማነታቸው አነጋግረናቸዋል ቀጥለን እናቀርብላችኋለን፡፡

“እግዚአብሔር የክብሩ መገለጫ እንደሚያደርገኝ አልተጠራጠርኩም” (ውብነሽ ለማ)

ውብነሽ ለማ ከ፳፻፲፭ ዓ.ም የግቢ ጉባኤያት ፍሬዎች መካከል አንዷ ናት፡፡ ከቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በመካኒካል ኢንጅነሪኒንግ ትምህርት ክፍል ሦስት ነጥብ ዘጠኝ ዘጠኝ (3.99) አጠቃላይ ውጤት በማምጣት የዩኒቨርሲቲው ዋንጫ እና ሁለት ሜዳልያዎች ተሸላሚ ለመሆን በቅታለች፡፡

ዝግጅት ክፍላችንም ስለ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም እና ግቢ ጉባኤ ቆይታዋ አነጋግረናታል፡፡

ውብነሽ ቆይታዋን ስትገልጽ “ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ተመድቤ ስሄድ ቦታው ገና አዲስ ስለ ነበር ፍርሃትና ግራ መጋባትም ገጥሞኝ ነበር፡፡ ነገር ግን ዓላማዬን ለማሳካት ምን ማድረግ አለብኝ ለሚለውና በኅሊናዬ ለሚመላለሰው ጥያቄ መልስ የሆነኝ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መኖርን ነው፡፡ እንደ ዓላማም አድርጌ የገባሁት ራሴን ውጤታማ ሆኜ መውጣትን ነው፡፡ እግዚአብሔር የክብሩ መገለጫም እንደሚያደርገኝ አልተጠራጠርኩም፡፡ ለዚህም መሸሸጊያ ያደረግሁት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ነው፡፡ ቦንጋ ስደርስም በአቅራቢያው ወደ ሚገኘው ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ነው የሄድኩት፡፡” በማለት ትውስታዋን አጋርታናለች፡፡

ጊዜ አጠቃቀሟን በተመለከተ ስትገልጽም፡- “ጊዜዬን በትምህርቴ፣ በጥናቴና በቤተ ክርስቲያን እንዲወሰን ማድረግ ቻልኩ፡፡ ቀድሞም በአካባቢዬ ባለው ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ አገለግል ስለነበር ሕይወቴን ከቤተ ክርስቲያን ጋር ማቆራኘት አልከበደኝም፤ ሌላም የሕይወት ተሞክሮ አልነበረኝም፡፡ በቅድመ ግቢ ጉባኤም ሆነ በዩኒቨርሲቲው ማኅበረ ቅዱሳን በሚሰጠው የግቢ ጉባኤ አገልግሎት ስሳተፍ ቆይቻለሁ፡፡ ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት በሰንበት ትምህርት ቤታችን ስንሸኝም የተመከርነው ምክር ስንቅ ሆኖኛል” ብላለች፡፡  

ጊዜዋን በአግባቡ መወጣት እንዳለባት ራሷን በማሳመን በዕቅድ በመመራት በተግባርም እንደፈጸመችው የምትገልጸው ውብነሽ ስለ ጊዜ እንዲህ ትላለች፡፡ “ጊዜን በተመለከተ ከቤተሰብ እንደመለየታችን መጠን በራሳችን ላይ የምንወስነው እኛው ብቻ ስለሆንን ነጻነት ይሰማናል፡፡ ብዙዎችም ለመዝናናትና ለማይጠቅሙ ነገሮች ጊዜያቸውን ስለሚያባክኑ ውጤታቸው ላይ ደካማ ሆነው ይገኛሉ፡፡ እኔ ግን ከትምህርቴ በኋላ ከቀኑ ፲ ሰዓት ጀምሮ የምገኘው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው፡፡ አጋጣሚ አስቸኳይ ነገር ሲገጥመኝ ግን በሌሊቱ ቤተ ክርስቲያን ተሳልሜ እመለሳለሁ፡፡ በነበረኝ ቆይታዬም ቤተ ክርስቲያን ሳልደርስ የቀረሁበት ጊዜ የለም፡፡ ከቤተ ክርስቲያን የተለየ ሕይወት ስለሌለኝ መብቴ ብቻ ሳይሆን ግዴታዬም አድርጌ ነው የቆየሁት፡፡ ከትምህርቴ፣ ከጥናት እና ከቤተ ክርስቲያን ውጪ የማሳልፈው ጊዜ ኖሮኝ አያውቅም፡፡

ስለ ጓደኛ ተጽእኖ ላቀረብንላት ጥያቄም “በአጋጣሚ ዓላማችን ተመሳሳይ የነበረ ዐራት ኦርቶዶክሳውያን ወንድሞችና እኅቶች ነበርን የተገናኘነው፡፡ በጣም ደስ የሚል ቅርበት ስለነበረን እንደጋገፋለን፣ አንዱ የሚያውቀውን ለሌላው ለማካፈል አይሰስትም፡፡ በጓደኛ ደረጃ ተሳክቶልኛል ማለት እችላለሁ፡፡ ያም ሆኖ ችግሮች አልነበሩም ማለት አይደለም፡፡ በተለይ የመጀመሪያ ዓመት ላይ በርካታ ዓይኖች ይፈትኑኝ ነበር፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ቸርነት ሁሉን አለፍኩት፡፡ ለዚህም ራሴን በሦስት ነገሮች መጥመዴ ጠቅሞኛል፡፡ በትምህርቴ፣ በቤተ ክርስቲያን(ግቢ ጉባኤ) እና ጥናቴ፡፡

በመማር ላይ ላሉና ወደፊት ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚገቡ ተማሪዎች ባስተላለፈችው መልእክትም “ዓላማቸውን መዘንጋት የለባቸውም፡፡ በኦርቶዶክሳዊነታቸውና በውጤታማነታቸው ከራሳቸው አልፈው የቤተሰቦቻቸው እና የቤተ ክርስቲያን ኩራት እንደሚሆኑ መገንዘብ አለባቸው፡፡ ማንኛውንም አስቸጋሪም ይሁን መልካም የሕይወት ውጣ ውረድ ቢገጥማቸው መሸሸጊያቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንደሆነች ማሰብ፣ በሯን ከፍታም እንደምትቀበላቸው አምነው መጠለል ይገባቸዋል፡፡ ክርስቲያን ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ምን ሕይወት አለው? ስለዚህ ተስፋ በመቁረጥ እንዳይዘናጉ፣ ከግል ጥረት ጋር እግዚአብሔርን መመኪያ አድርጎ መጓዝ ይጠበቅባቸዋል” በማለት ከተሞክሮዋ አካፍላናለች፡፡

በቀጣይ በክፍል ሁለት ዝግጅታችን ደግሞ የሌሎችን ኦርቶድክሳውያን ውጤታማ ተመራቂዎች ተሞክሮዎችን ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡ ይቆየን፡፡

የአዲስ አበባ ማእከል በግቢ ጉባኤያት ያስተማራቸውን ተማሪዎች አስመረቀ

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ከመደበኛ ትምህርታቸው በተጨማሪ የቅድሰት ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ትምህርት ተከታትለው ያጠናቀቁ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፮፻ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ሐምሌ ፲፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽርሐ ተዋሕዶ አዳራሽ በድምቀት አስመረቀ፡፡

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል የተጀመረ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳንን በመወከል ከሥራ አመራር ጀምሮ በልዩ ልዩ ማስተባበሪያዎች ለረጅም ዓመታት በማገልግል የሚታወቁት በአሁኑ ወቅት የሕብረት ባንክ ም/ፕሬዚዳንት የሆኑት በኩረ ትጕሃን አንዱዓለም ኃይሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ በመልእክታቸውም፡- “መመረቃችሁ አዲስ የሕይወት ምዕራፍ የምትጀምሩበትና ሥራ ለመቀጠርና በጋራ ሆናችሁ ሥራ የምትፈጥሩበት ጊዜ ላይ ደርሳችኋል፡፡ የምታገኟቸውን ዕድሎች መጠቀም፣ ራሳችሁን ማሳደግና በሙያችሁ ብቃት ያላችሁ (  Profesional) ሁኑ፤ ከሁሉም በላይ ግን ፈቃደ እግዚአብሔርን አስቀድሙ” በማለት ከሕይወት ተሞክሯቸው ተነሥተው ለተመራቂዎች ምክርና መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ አካል ከነበሩት ውስጥ አንዱ የዕለቱ ትምህርት ወንጌል ሲሆን በመ/ር ኢዮብ ይመኑ “ሌላ ሸክም አላሸክማችሁም፤ ነገር ግን እስክመጣ ድረስ ያላችሁን ጠብቁ” (ራእ.፪፥፳፭) በሚል ርእስ ለተመራቂዎች ለወደፊት ሕይታቸው ሥንቅና መመሪያ የሚሆን ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አባባ ማእከል ጸሐፊ የሆኑት አቶ ካሣሁን ኃይሌ በኩላቸው ባስተላለፉት መልእክትም “በየጊዜው ማኅበራችሁ ማኅበረ ቅዱሳን እናንተን በማስተማር፣ በመምከር፣ የሕይወት አቅጣጫዎችን በመጠቆም፤ የታተሙ መጻሕፍትን እና ጽሑፎችን በማዳረስ መንፈሳዊ ምግብ እንድትመገቡ ሲያደርግ ቆይቷል፤ እንዲሁም በመደበኛው ትምህርታችሁ እንድትበረቱ ሐሳብ በመስጠት፣ በመደገፍ ንስሓ ገብታችሁ የምሥጢራት ተካፋይ እንድትሆኑ በማድረግ በሕይወታችሁ ላይ ለውጥ አምጥታችኋል” ብለዋል፡፡

አቶ ካሳሁን ከተመራቂዎች የሚጠበቅባቸውን ሲገልጹም “በምትሄዱበት ሁሉ በመንፈሳዊ ሕይወት ራሳችሁን እያነጻችሁ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባስታጠቀቻችሁ መንፈሳዊ ትጥቅ ሌሎችን በማጽናት በተለይም በልዩ ልዩ ጭንቀት ውስጥ ያለውንና መድረሻ አጥቶ የሚባዝነውን ትውልድ ትታደጉ ዘንድ መትጋት ይጠበቅባችኋል፡፡” ሲሉ የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በተመራቂዎች የቀረቡት የበገናና እና የያሬዳዊ ወረብ፣ እንዲሁም የልዩ ፍላጎት ተመራቂዎች ያቀረቧቸው መንፈሳዊ ዝማሬዎች የመርሐ ግብሩ ልዩ ድምቀት ነበሩ፡፡ በምረቃ መርሐ ግብሩም ላይ ተመራቂዎች፣ የተመራቂ ቤተሰቦች፣ የማኅበረ ቅዱሳን ማስተባበሪያ ኃላፊዎች፣ የግቢ ጉባኤያት መምህራንና የተመራቂዎቹ የንስሓ አባቶች የተገኙ ሲሆን ለተመራቂዎች የአደራ መስቀል በካህናት አባቶች ተባርኮ ተበርክቶላቸዋል፡፡

«ታገኙ ዘንድ ሩጡ» (፩ኛቆሮ.፱፥፳፬)

በመ/ር ተርቢኖስ ቶሎሳ 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በግሪክ ከነበሩ አውራጃዎች አንዷ ከሆነችው አካይያ መዲና ቆሮንቶስ ከተማ ገብቶ ለሕዝቡ ጌታ ከፅንሰቱ ጀምሮ ያደረገውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ ቢነግራቸው ብዙዎቹ ከጣዖት አምልኮ እግዚአብሔርን ወደ ማምለክ፣ ኃጢአትን ከመሥራት ጽድቅን ወደ ማድረግ ተመለሰው፤ አምነው ተጠመቁ፡፡ (ሐዋ.፲፰፥፩–፲)

ቅዱስ ጳውሎስ የቆሮንቶስ ከተማን ሕዝብ አስተምሮ፣ አሳምኖና አጥምቆ ካቆረባቸው በኋላ ከዚያ ወጥቶ ወደ ኤፌሶን ሄደ፡፡ ነገር ግን በቆሮንቶስ ያሉ ምእመናን «አስተምሮ ዋጋ ይቀበላል (ገንዘብ ይበላል)» ብለው አሙት፡፡ ይህንን ሐሜታቸውን ሰምቶ ተስፋ ሳይቆርጥ የወንጌል አገልግሎቱን፣ ማለትም መንፈሳዊውን ትምህርት በሰፊው ቀጥሎበት ለቁመተ ሥጋ ያህል በምእመናን ገንዘብ መመገብ ምንም ቁም ነገር እንዳልሆነ፣ ምንም ሥጋዊ ጥቅም እንደማይፈልግና ገንዘብም እንዳልተቀበላቸው በትምህርቱ ውስጥ ይገልጥ ነበር፡፡ ይልቁንም ቅዱስ ጳውሎስ ይተጋ የነበረው ወንጌልን ስለማስተማር፣ ሰዎችንም ለድኅነት ለማብቃት እንደ ሕጋቸው፣ እንደ አኗኗራቸው ሁሉ እየኖረ ወንጌልን በመስበክ በዓለም በሚደረግ ሰልፍ፣ ሩጫና ሽልማት እየመሰለ ከክርስትና የሚገኘውን ክብር አስተምሯቸዋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ «በእሽቅድምድም ሥፍራ የሚሽቀዳደሙ ሁሉ እንደሚፋጠኑ አታውቁምን? ለቀደመው የሚደረግለት ዋጋ አለ፤ እንዲሁ እናንተም እንድታገኙ ፈጽማችሁ ሩጡ» ይላል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፱፥፳፬) በጦር ሜዳ ተሰልፎ እየፎከረ፣ ጠላቱን ድል የሚያደርግ አርበኛ (ጦረኛ) ከጌታው ዘንድ ሹመት፣ ሽልማት እንዲያገኝ እንዲሁ መንፈሳዊ አርበኛ የሚሆኑ ምእመናንም በምግባር በትሩፋት እየተሸቀዳደሙ ዋጋቸውን (ክብራቸውን) ያገኙ ዘንድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አጥብቆ ይመክራቸዋል፡፡

መሮጥና ማግኘት የሚሉትን ፀንሰ ሐሳቦች ሐሳብ በሁለት መንገድ ማየት እንችላለን፡፡ አንደኛው፡- በዚህ ዓለም በሚደረግ የሩጫ ውድድር አንጻር በክርስትና የሚደረግ የሕይወት ዕድገትና መንፈሳዊ ፉክርክር ነው፡፡ አትሌቶች ሀገራቸውን ወክለው በሩጫ ተወዳድረው አሸናፊ ሆነው ተሸልመው የራሳቸውንም የሀገራቸውንም ስም በዓለም ያስጠራሉ፤ ሥጋውያን ሯጮጭም ሲሮጡ በመንገዳቸው ላይ የሚደርስባቸውን ድካም የሚገጥማቸውንም መሰናክል ተቋቁመው የሚያልፉትና ለአሸናፊነት የሚበቁት በአሸናፊነታቸው የሚያገኙትን ክብርና ሽልማት ተስፋ በማድረግ ነው፡፡ ይህንንም ተስፋ ሳይጠራጠሩ እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት ይሮጣሉ፡፡

መንፈሳውያን ሯጮች የሆኑ ምእመናንም እንዲሁ በኅሊናቸው ከዚህ ዓለም ድካምና ፃዕር በኋላ ያለውን የዘለዓለም ሕይወትና የማያልፍ ተድላ ደስታን እያሰቡ ወደ መንግሥተ ሰማያት በእግረ ኃሊናቸው በጽናት ይሮጣሉ፡፡ በሕይወት መንገዳቸው ላይ ከፈቃደ ሥጋቸው፣ ከአጋንንትና ከዐላውያን ነገሥታት ሁሉ የሚደርስባቸውን የቅድስና ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ሩጫ መሰናክሎችን በፍጹም እምነትና በጽናት አሸንፈው በእግዚአብሔር ዘንድ የዘለዓለማዊው ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ተሸላሚ ይሆናሉ፡፡

ክርስቲያን ሁል ጊዜም በምግባረ ክርስትና የሚሮጥ (የሚያድግ) ነው፤ ምግባረ ክርስትና እግዚአብሔርን የምንመስልበት ሕይወት ነው፡፡ ሐዋርያው «እኔ ክርስቶስን እንድመስለው እናንተም እኔን ምሰሉ» እንዳለ፡፡ (፪ኛቆሮ.፲፩፥፩) በጥንተ ፍጥረትም አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር «ሰውን በአርአያችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠር>> ብሎ እርሱን የመምሰል ሕይወት በሰው እንደሚገለጥ ተናግሯል፡፡ (ዘፍ.፩፥፳፮) እግዚአብሔር ደግሞ በባሕርዩ መልካም ነው፤ ለመልካምነቱም ገደብ የለውም፡፡

ምግባረ ክርስትና ገደብ የለውም፤ ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡ እስከ አሁን የጾምኩት፣ የጸለይሁት፣ ያስቀደስኩት፣ የቈረብኩት ይበቃኛል፣ … አይባልም፡፡ ምክንያቱም የምንነሣበት እንጂ የምንደረስበት ምግባር የለምና፣ በጎነት መጨረሻ የለውም፡፡ ስለዚህ የክርስቲያን ኑሮው ሁል ጊዜ በሩጫ (በበጎ ምግባር መገሥገሥ) ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ «በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እጄን እዘረጋለሁ» ያለውም ለዚህ ነው፡፡ (ፊል.፫፥፲፫) ተክል እንደተተከለ ብቻ ከቀረ ይደርቃል እንጂ አያድግም፡፡ ስለዚህ አድጎ ፍሬ እንዲያፈራ ይኮተኮታል፤ ከአፈር፣ ከአየር እና ከውኃ ይመገባል፡፡  ከዚህም የተነሣ አድጎ፣ ለምልሞና አብቦ ያፈራል፤ ክርስቲያናዊ ሰውም እንዲሁ ነው፡፡ በሃይማኖትና በጥምቀት፣ ይተከላል፤ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይመገባል፤ በምግባር ለምልሞ፣ በትሩፋት አብቦ የክብር ፍሬ ያፈራል፡፡ ስለዚህ በክርስትና ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡

በክርስትና ሕይወት ውስጥ ምግባር ሃይማኖት «እዚህ ጋር ይበቃኛል» ብለን የምናቆመው ሳይሆን ዕለት ዕለት መሽቀዳደም፣ ለፍቅር፣ ለየዋሀት፣ ለቅንነት፣ ለለጋሥነት፣ ለርኅራኄ … መፎካከር ነው፡፡ ሐዋርያው «ፍቅርን ተከተሏት>» በማለት እንዳስተማረን፡፡ (፩ኛቆሮ.፲፬፥፩) እንዲህ ከሆነ በሰማይ የሚገኘው ክብር ታላቅ ነው፡፡ ክብር ሁሉ በሥራ መጠን ነውና ለሁሉም እንደ ዋጋው እከፍለዋለሁ እንዳለው አምላካችን ጥቂት የሠራ ጥቂት ክብር ይቀበላል፤ አብዝቶ የሠራም አብዝቶ ይቀበላልና፡፡ (ራእ.፳፪፥፲፪)

ሁለተኛው በጦር ሰልፍ በሚደረግ ሩጫ አንጻር በተጋድሎ የሚገኝ ጸጋን ለማመልከት ነው፡፡ ከላይ እንዳየነው የጦር ሰልፍ ሩጫ ጠላትን ድል አድርጎ ነፃነትን ማወጅ፣ ከድል በኋላ የሚገኝን ሹመትንና ሽልማትን ገንዘብ ማድረግ፣ ክብርንና አዎንታዊ የታሪክ ባለቤት መሆንን መቀዳጀት ነው፡፡ ስለዚህ ሥጋውያን ጦረኞች እግራቸውን ለጠጠር፣ ግንባራቸውን ለጦር ሰጥተው ከድል በኋላ ስለሚያገኙት ሽልማት እኔ ልዝመት እኔ ልዝመት ብለው ይሽቀዳደማሉ፡፡

ከተጋድሎ በኋላ የሚያገኘውን ክብር የሚያስብ ክርስቲያንም እንደዚሁ ዲያብሎስ ያሰለፈውን ጦር ድል ለመንሣት ይሰለፋል፣ ሞትንም አይፈራም፡፡ «ብእሲ ዘይሬኢ አክሊላቲሁ ኢይሜምእ፤ አክሊሉን የሚያይ ሰው ወደ ኋላ አያፈገፍግም» በማለት እንዳስተማረን፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ተግሣጽ) ከፊቱ የሚጠብቀውን ክብርና ሽልማት የሚያስብ ተጋዳይ በአሁናዊ መከራው አይማረርም፡፡ መዝሙረኛው ዳዊት እንዲህ ይላል «እለ ይዘርዑ በአንብዕ ወበሐሴት የዐርሩ፤ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ ወጾሩ ዘርዖሙ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ ወጾሩ ከላስስቲሆሙ፤ በልቅሶ(በዕንባ) የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ፤ በሄዱጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዷቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ» እንዲል፡፡ (መዝ.፻፳፭፥፮-፰)

በክረምት የሚዘራ ገበሬ ጠዋት ሲወጣ በላይ ዝናቡ ይወርድበታል፤ በታች ቅዝቃዜው፣ ጭቃውና ጎርፉ ይፈራረቁበታል፤ ስለዚህ በመከራ ይዘራል፡፡ የዘራው አፍርቶ አጭዶ ሲከምረው ግን መከራውን ረስቶ ጨምሬ ዘርቼ ቢሆን ኖሮ ይላል፤ እሸቱን እየበላ ነዶውን ሲሰበስብም ደስ ይለዋል፡፡ እንዲሁ በክርስትና ሕይወታቸው የጸኑ ሰማዕታት ከተሳለ ስለት፣ ከነደደ እሳት ሲገቡ መከራው ይሰማቸዋል፤ ጻድቃን ፍትወታት እኩያት ኃጣውእ ርኵሳት ሕሊናቸውን ያስጨንቃቸዋል፣ ድል ከነሡ በኋላ ግን ሰማያዊ አክሊልን ተቀዳጅተው በተድላ በደስታ ይኖራሉ፡፡

ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ በአካለ ነፍስ ሆኖ መነኮሳት በአክናፈ እሳት ወደ ኢየሩሳሌም ሲገቡ አይቶ አንድን አባት «ሰላም ለክሙ ብፁዓን መነኮሳት፤ ንዑዳን ክቡራን መነኮሳት ሆይ ሰላም ለእናንተ ይሁን»  አለው፡፡ መነኮሱም «አንተም እንጂ ንዑድ ክቡር ነህ በዘመንህ ቀርነ ሃይማኖት ቆሞልሀልና» አለው፡፡ ቆስጠንጢኖስም «ይህንን አውቄስ ቢሆን መንግሥቴን ትቼ እንደ እናንተ በምናኔ በኖርሁ ነበር» ብሎታል፡፡ (ፊልክስዩስ) ስለዚህ የዚህን ዓለም መከራና ሥቃይ የወዲያኛውን ክብር ያስረሳዋል፡፡ በዚህ ዓለም ሴት ልጅ በጭንቅና በምጥ ስትወልድ ታዝናለች ከወለደች በኋላ ግን ደስ ይላታል፤ ከወደለች በኋላ ግን ጭንቋንና ምጧን አታስበውም፤ ምክንያቱም ጨንቋንና ምጧን በልጇ ስለምትረሳው፡፡ (ዮሐ.፲፮፥፳፩) ስለዚህ ክርስቲያኖችም የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ በተጋድሎና በትዕግሥት ሊያልፉት ይገባል፡፡ እንዲህም ከሆነ በሰው ኅሊና የማይተረጎም ሰማያዊ ክብርን ያገኛሉ፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ «እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወት አክሊልንም እሰጥሀለሁ» እንዲል፡፡ (ራእ.፫፥፲) ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት በተጋድሏቸውና በአሸናፊነታቸው ከሚቀበሉት ክብር አንጻር አሁን የሚያገኛቸው መከራ ኢምንት ነው፡፡ ስለዚህ ሰማያዊውን ክብር ለማግኘት መንፈሳዊውን ሩጫ መሮጥ ከኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር፡፡

ክርስቲያናዊ ሕይወት ከግቢ ጉባኤያት በኋላ

በመ/ር ተመስገን ዘገዬ

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከብዙ ውጣ ውረድ ማለትም ዓለማዊና መንፈሳዊ ትምህርታቸውን በአግባቡ ከተማሩ በኋላ ተመርቀው ሲወጡ እንዴት መኖር እንደለባቸውና ምን ማድረግ እንደሚገባቸው በዚህ ጽሑፍ ለማሳየት እንሞክራለን፦

፩. ከወንድሞች ጋር በኅብረት መኖር 

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በተሰማሩበት ሁሉ ከማኅበረሰቡ ጋር በኅብረት መኖሩ መልካም ነው፡፡ ክርስትና የኅብረት እንጂ የብቸኝነት ሩጫ አይደለችም፡፡ መጽሐፍም «ወንድሞች በሕብረት ቢቀመጡ እነሆ መልካም ነው፤ እነሆም ያማረ ነው» ሲል መናገሩም ይህንን ያስረዳል፡፡ (መዝ.፻፴፫፥፩)

ጠቢቡ ሰሎሞንም «ድካማቸው መልካም ዋጋ አለውና አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን ይሻላል፡፡ አንዱ ቢወድቅ ሁለተኛው ያነሣዋልና፤ አንድ ብቻውን ሆኖ በወደቀ ጊዜ ግን የሚያነሣው ሁለተኛ የለውምና ወዮለት፡፡» ብሎ እንደተናገረው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በዚህ ዓለም ሲኖሩ በብዙ መንገድ መደጋገፍ ያሻቸዋል፡፡ (መክ.፬፦፱) አንዱ ለሌላው መሥዋዕት  እስከ መሆን ድረስ  አብሮ በፍቅር  መኖር ይገባል፤  የክርስትና ትርጉሙ ይህን  ነውና፡፡ የሞላለትና በሁሉ  ምሉዕ  የሆነ ሰው በዚህ ዓለም ማግኘቱ አስቸጋሪ ሊሆን ስለሚችል መደጋገፍ፣ መረጃ መለዋወጥ  ያስፈልጋል፡፡

በአንድነት መኖር በኢኮኖሚም ለመደጋገፍ፣ እንዲሁም ከተለያዩ የውስጥና የውጭ ፈተናዎች ለመከላከል፣ እንዲሁም ለመጠበቅ ይረዳል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን «ብረት ብረትን ያስለዋል፤ ሰው ባልንጀራውን ይስለዋል፡፡» በማለት መልካም ጓደኛ ሌላውን ጥሩና የተስተካከለ ሰው እንዲሆን እንደሚረዳው ተናግሯል፡፡ (ምሳ.፳፯፥፲፮) መተራረም የሚቻለው በመከባበርና መልካሙን መንገድ በመከተል፤ አንተ ከእኔ ትሻላለህ በመባባል የተሰጠውን አስተያየት በመጠቀም የሕይወት ለውጥ ማምጣት ሲቻል ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት «ከቸር ሰው ጋር ቸር ሆነህ ትገኛለህ፤   ከቅን ሰው ጋር ቅን ሆነህ ትገኛለህ፤ ከንጹሕ  ጋር ንጹሕ  ሆነህ ትገኛለህ» እንዲል፡፡ (መዝ.፲፯፥፳፭)

፪. በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ተካፋይ መሆን፡-

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ የምታድላቸው ሰባት ሀብታት (ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን) አሏት፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን «ጥበብ ቤትዋን ሠራች፥ ሰባቱንም ምሰሶችዋን አቆመች። ፍሪዳዋን አረደች፥ የወይን ጠጅዋን ደባለቀች፥ ማዕድዋን አዘጋጀች። ባሪያዎችዋን ልካ በከተማዪቱ ከፍተኛ ሥፍራ ላይ ጠራች። አላዋቂ የሆነ ወደዚህ ፈቀቅ ይበል፤ አእምሮ የጐደላቸውንም እንዲህ አለች። ኑ፥ እንጀራዬን ብሉ፥ የደባለቅሁትንም የወይን ጠጅ ጠጡ። አላዋቂነትን ትታችሁ በሕይወት ኑሩ፥ በማስተዋልም መንገድ ሂዱ።» በማለት ይገልጻል፡፡ (ምሳ.፱÷፩-፭) በዚህ ቃለ ትንቢት መሠረት ጥበብ የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ቤት የተባለችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ እንዲሁም የክርስቲያኖች ሰውነት ናት፤ ሰባቱ ምሰሶዎች የሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናቸው። የታረደው ፍሪዳ ቅዱስ ሥጋው፣ የተደባለቀው ወይን የክቡር ደሙ ምሳሌ ነው።

በቅዱስ ወንጌል «ኢየሱስም፡- ‘ኑ፥ ምሳ ብሉ’ አላቸው። ከደቀ መዛሙርቱ አንተ ማን ነህ? ብሎ ሊጠይቀወ የደፈረ የለም፤ ጌታችን እንደሆነ አውቀዋልና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መጣና ኅብስቱን   አንሥቶ ሰጣቸው፥ ከዓሣወም እንዲሁ።» ተብሎ እንደተጻፈ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በምንችውለውና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በሚፈቅድልን መሠረት በአገልግሎት መሳተፍ ይጠበቅብናል፡፡ ገና በሥራ ቦታ ተመድበን እንደሄድንም የንስሓ አባት መያዝ፣ በየጊዜው ንስሓ መግባትና እየተገናኘን ቀኖና ተቀብለን ሥጋ ወደሙን መቀበል ያስፈልገናል፡፡ (ዮሐ.፳፩፥፲፪)

በሕይወታችን «የበይ ተመልካች» መሆን አያስፈልግም፡፡ «እውነት እውነት እላችኋለሁ የሰውን ልጅን ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፤ … ሥጋዬን   የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል፤ እኔም በእርሱ እኖራለሁ» እንደተባለ ክርስቲያን  የሆነ ሁሉ  ከዚህ ምሥጢር  በየጊዜው  መሳተፍ  እንዳለበት መረዳት ይገባል፡፡ (ዮሐ.፮፥፶፫-፶፮)

የምንሠራቸው ሥራዎች የሚባረኩት በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምናድገው፣ መንግሥቱንም መውረስ የምንችለው ቅዱስ ሥጋውን ስንበላ፣ ክቡር ደሙንም ስንጠጣ ብቻ ነው፡፡ የምሥጢራት ተካፋይ በመሆን ሌሎችም እንዲካፈሉ ማድረግ ይኖርብናል፡፡

፫. ኑሮን በዕቅድ መምራት፡-

ዕቅድ የሌለው ሁሉ መንገዱ ውጣ ውረድ የበዛበት ነው፡፡ ኑሮዬ ይበቃኛል ብለን መኖር የምንችለው በዕቅድ ስንመራ ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «ስለ ጉድለት አልልም የምኖርበት ኑሮዬ ይበቃኛል ማለትን ተምሬለሁ» ያለው ክርስቲያን ሕይወቱን እንደዚሁ በዘፈቀደ እንደመጣለት መምራት እንደማይገባው ሲያስገነዝበን ነው፡፡ (ፊል.፬፥፲) ዕድሜያችን በዕቅድ ላይ ተመሥርተን በመምራት ካልተጠቀምንበት ምንም ሳንሠራበት ያልቃል፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረቱን ሲፈጥር በአንድ ጊዜ ማከናውን የሚችለውን ስድስት ቀናት የፈጀበት እያንዳንዱን ነገር በዕቅድና በሥርዓት ማከናወን እንደሚገባ ሲያስተምረን ነው፡፡ ሥራ የምንሠራበት፣የምንጸልይበት፣ ትምህርተ ሃይማኖት የምንማርበት፤ ንስሓ ገብተን ቅዱስ ቊርባኑን የምንቀበልበት የራሳችን  ዕቅድ ያስፈልገናል፡፡

የምናገኘው ገንዘብ ያለ ዕቅድና ዓላማ የምናወጣ ከሆነ ከወር ወር መድረስ አንችልም፡፡ ደመወዛችን የተቀበልን ሰሞን ሆቴል የምናማርጥ ከሆነ በወሩ አጋማሽ ጾማችንን ማደራችን የማይቀር ጉዳይ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «ነገር ግን ሁሉ በአገባብና በሥርዓት ይሁን» ይላል (፩ኛቆሮ.፲፬፥፵) የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር የቄሣርን ለቄሣር እንደተባለ በእግዚአብሔር ድርሻ ላይ ታማኞች መሆን አለብን፡፡ ስለሆነም በበረከት እንዲያትረፈርፈን ዐሥራት የማውጣት ልምድ  ከመጀመሪያው ደመወዛችን መጀመርና በየወሩ ዐሥራታችንን ማውጣት ይኖርብናል፡፡

፬. በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በአገልግሎት መሳተፍ

ልዑል እግዚአብሔርን ማገልገል የምንችለው በቤተ ክርስቲያን ሲሆን በዕውቀታችን፤ በጉልበታችን፤ በገንዘባችንና በጊዜያችን ሁሉ እግዚአብሔርን ማገልገል ይጠበቅብናል፡፡አንዳንዶች ለምን አታገለግሉም ሲባሉ የማይረባ ምክንያት እየደረደሩ ከቤተ ክርስቲያን ይርቃሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ እንዲለመኑ፣ «እባካችሁ» እንዲባሉ ይፈልጋሉ፡፡ በማገልገላችን ከኃጢአት እንጠበቃለን፣ ሰላምና ተስፋ የተሞላበት ኑሮ እንኖራለን፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም «ስለዚህ ወንድሞቼ ሆይ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታፀኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉም» በማለት በአገልግሎት መትጋት እንደሚገባን ይመክረናል፡፡ (፩ኛጴጥ.፩፥፲)

ብዙዎች ከተመረቅን በኋላ አገልግሎት ያለ አይመሰለንም፡፡ አገልግሎታችንም ግቢ ጉባኤ ላይ ብቻ ይቀራል፡፡ ይህ ደግሞ የክርስትናውን ምሥጢር በአግባቡ አለማወቅ ነው፡፡ ጌታችንም ስለ ለቅዱሳን ሐዋርያት ስለ ነገረ ምጽአቱ ሲያስተምራቸው «እስከ መጨረሻው የሚጸና ግን እርሱ ይድናል» እንዳላቸው ግቢ ጉባኤ ብቻ በማገልገላችን የምንድን አይደለንም፤ እስከ መጨረሻው የሕይወት ፍጻሜ ድረስ ቃሉን በመጠበቅና በማገልገል መጓዝ እንጂ፡፡ (ማቴ.፳፬፥፲፫) የሕይወት አክሊልንም ለመቀበል እስከ መጨረሻው መትጋት ያስፈልጋል፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም  «ትቀበለው ዘንድ  ስላለህን መከራ ምንም አትፍራ፤ እነሆ እንድትፈተኑ ሰይጣን ከእናንተ አንዳንዶችን ወደ እሥር ቤት እንዲገቡ ያደርጋል፡፡  ዐሥር ቀንም መከራ ትቀበላላችሁ፤ እስከ ሞት ድረስም የታመንህ ሁን የሕይወት አክሊልንም እሰጥሃለሁ» ይላል፡፡ (ራዕ.፪፥፲)

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚገኙ መዋቅሮች ማለትም በሰ/ት/ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ በመታቀፍ ማገልገል ይገባል፡፡ በተለይም ለአገልግሎት   የሚመች ሰበካ ጉባኤ እንዲመሠረትና በዚያም ውስጥ የራስን አሻራ በማሳረፍ ቤተ ክርስቲያንን መደገፍ፣ የተሻለና ቀልጣፋ አሠራርን መከተል የሚያስችሉ መንገዶችን በመቀየስ የድርሻን መወጣት ያስፈልጋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በተመረቁበት የሙያ መስክ ገብተው አስፈላጊውን ሥራ መሥራት ብቻ በቂ አይደለም፡፡ በታማኝነትና በቅንነት መሥራትንም ይጠይቃል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ሁኔታ በአሁኑ ጊዜ የልጆቿችን ሙያ እንደምትሻ ግልጥ ነው፡፡ በተለይም የልማት ተቋማትን በማደራጅት (ለምሳሌ ፕሮጀክት በመቅረጽ) በኩል ያለባትን የመዋዕለ ንዋይ  ችግር ለመቅረፍ የምትወስዳቸው ርምጃዎች ማንነቷን የሚያሳውቁ እንጂ የሚያደበዝዙ እንዳይሆኑ  በውስጧ ሆነው ምሥጢሯንና  ቋንቋዋን የሚያውቁ የራሷ ልጆች ቢያጠኑላት ዛሬ የሚታዩት አስተዳደራዊ ችግሮች ባልተከሠቱ  ነበር፡፡

ተመርቀን ከየግቢ ጉባኤያት ተለይተን ወደ ሥራ ዓለም ስንሠማራ እንደ የአካባቢው ነባራዊ ሁኔታ በተለያዩ ደረጃዎች ላይ ያሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያጋጥሙናል፡፡ ተጠናክረው በጥሩ አገልግሎት የሚገኙ፣ ተቋቁመው በአገልጋይ እጥረት ምክንያት አገልግሎት ያቆሙ፣ እንዲሁም ያልተቋቋሙባቸው አካባቢዎች ሊያጋጥሙን ይችላል፡፡ ከጠንካሮቹ ሰ/ት/ቤቶች ልምድ በመውሰድ የሚጠናከሩበትን መንገድ ማሰብ፣ መቀየስና ተግባራዊ እንዲሆን የተቻለውን ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ በግቢ ጉባኤያት ካገኘናቸው ልምዶችም በመነሣት ስልት መቀየስ ከግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡

በየሄድንባቸው አካባቢዎች ሰ/ት/ ቤት ከማቋቋማችን በፊት አስቀድመን አካባቢውን ሕዝብ ጠባዩን ፍላጎቱን ባህሉንና የኗኗር ዘይቤውን ማጥናት ያስፈልጋል፡፡ ማጥናት፣ ከዚያም በቃለ ዓዋዲው መሠረት ማደራጀት እንዳለብን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ብዙ ከመናገር ብዙ መስማትና ከማገልገልም በፊት ብዙ መገልገልን መምረጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ያለውን ሁኔታ ሳናጠና በድፍረት መግባት መውጫችንን ያከብደዋልና፡፡ «እንደ እባብ ብልህ እንደ ርግብ የዋህ» መሆን ያስፈልጋል፡፡(ማቴ.፲፥፲፮) በተቻለ መጠን እኛ እንደ ወንድምና እኅት ቀርበን የሥጋዊ ሕይወታችን አለመሟላት መንፈሳዊና ሕይወታችንን እንደሚያጎድለው ብዙዎችም ወደ መጥፎ ሕይወት እንዳይገቡ ማሰገንዘብ አለብን፡፡

“ለፍጥረትም ሁሉ ወንጌልን ስበኩ” (ማር. ፲፮፥፲፭)

በእንዳለ ደምስስ

ይህንን ቃል ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሞቱ ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገለጠው በሌሊት ፈጥነው ወደ መቃብሩ ላመሩት ለመግደላዊት ማርያም እና እርሷን ተከትለው ለመጡት ሴቶች ነበር፡፡ ወደ መቃብሩም በደረሱ ጊዜ ሁለት መላእክት ተገልጠውላቸው መግደላዊት ማርያምን “አንቺ ሴት ምን ያስለቅስሻል?” አሏት፡፡ እርስዋም “ጌታዬን ከመቃብር ውስጥ ወስደውታል፤ ወዴትም እንደወሰዱት አላውቅም” አለቻቸው፡፡

ይህን ተናግራ ወደ ኋላዋ መለስ ስትል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቆሞ አየችው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም እንደሆነ አላወቀችም፡፡ … “አትንኪኝ፤ ወደ አባቴ አላረግሁምና ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሂጂና ወደ አባቴ ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬ ወደ አምላካችሁም አርጋለሁ አለ ብለሽ ንገሪያቸው” አላት፡፡

ማርያም መግደላዊት እና ሴቶቹም ፈጥነው ሄደው ሐዋርያት ተስፋ ቆርጠው በአንድነት ተሰብስበው እያዘኑና እያለቀሱ ሳሉ መግደላዊት ማርያም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መነሣት የምሥራች ነገረቻቸው፡፡ ነገር ግን አላመኗትም፤ ተረትም መሰላቸው፡፡ ሉቃስ እና ቀለዮጳም ተስፋ ቆርጠው ወደ ኤማሁስ ሲሄዱ እንደተገለጠላቸው ለሐዋርያቱ ምሥክርነት ቢሰጡም ሊያምኑ አልቻሉም፡፡ ከዚህ በኋላ ዐሥራ አንዱ ሐዋርያት በሐዘንና በትካዜ ውስጥ ሆነው ሳሉ ጌታችም መድኃኒታችን ኢሱስ ክርስቶስ በመካከላቸው ተገኝቶ ራሱን ገለጠላቸው፡፡

በመጨረሻም “ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፣ ለፍጥረትም ሁሉ ወንጌልን ስበኩ” በማለት ከተናገራቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ (ማር. ፲፮፥፲፭፤ ማቴ. ፳፰፥፩-፲፤ ሉቃ. ፳፬፥፩-፳፯)፡፡

ይህ ትእዛዝ ለሐዋርያት ብቻ ሳይሆን ከእነርሱ በኋላ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ለሚነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ መምህራንና ቃሉን ሰምተው አምነው ለሚያስተምሩ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዋስ ጠበቃ ለሆኑ ሁሉ ነው፡፡ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን ያመሰግኑ ዘንድ እንዲሁ ብርሃናችሁ በሰው ፊት ይብራ” ተብሎ እንደተጻፈ ጨለማውን ዓለም በወንጌል ብርሃንነት ተመርተው እንቅፋቱን ሁሉ ማስወገድ፣ እንደሚገባ ያስገነዝበናል፡፡ (ማቴ. ፭፥፲፬-፲፮)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ክርስቲያኖችን ያሳድድ፣ ይገርፍና ያሠቃይ እንደነበር፤ ከዚያም አልፎ ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስን አይሁድ በድንጋይ ሲወግሩት የገራፊዎችን ልብስ እስከ መጠበቅ የደረሰ እንደ ነበር ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ ነገር ግን ያ ሁሉ አልፎ የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ምርጥ ዕቃ” እስከ መሆን ደርሷል፡፡ “ተነሥና ሂድ፤ በአሕዛብና በነገሥታት በእስራኤል ልጆችም ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ አድርጌዋለሁና” እንዲል፡፡ ሳውል የተባለው ቅዱስ ጳውሎስም ወንጌል በዓለም ሁሉ ይዳረስ ዘንድ ሳይታክት እያስተማረና እየገሠጸ በአገልግሎቱ ጸንቶ ሰማዕትነትን እስኪቀበል ድረስ ለአምላኩ ታምኗል፡፡ (ሐዋ. ፯፥፶፬-፷፤ ፱፥፲፭)

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሆነን የእግዚአብሔር ማዕድ ከመደበኛው ትምህርት በተጨማሪ ተዘርግቶ ይጠብቀናል፡፡ በተመቻቸ ሁኔታ ውስጥ ሆነን ጊዜአችንን ብቻ መሥዋዕት በማድረግ የእግዚአብሔርን ቃል ለመማር የሚያቅተን ብዙዎች ነን፡፡ ለመማር ፈቃደኞች ሆነን ብንመጣም ከግቢ ተመርቀን ስንወጣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በክብር እንደተቀበለችን በክብር በአባቶች ቡራኬና መስቀል ባርካ ወደ ዓለም ስትልከን ስንቶቻችን እንሆን የተሰጠንን አደራ የምንወጣው?

ከግቢ ወጥተን ወደ ማኅበረሰቡ ስንቀላል ዓለም የራሷን ዝግጅት አድርጋ ትጠብቀናለች፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም “ልጆቼ ኑ፣ የሰጠኋችሁን አደራ ትወጡ ዘንድ ጊዜው ደርሷልና በደረሳችሁበት ሁሉ  መልካም የሆነውን አድርጉ” ትለናለች፡፡ የትኛውን ነው የምንመርጠው? እንደ ዴማስ መኮብለለን ወይስ እንደ ጢሞቴዎስ ታምኖ ማገልገል? ጢሞቴዎስ ወንጌሉን ከማን እንደተማረ ያውቃልና ለአምላኩም፣ ለመምህሩም ታምኖ ተገኘ፡፡ “አንተ ግን በተማርህበትና በተረዳህበት ነገር ጸንተህ ኑር፤ ከማን እንደተማርኸው ታወቃለህና፡፡” ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ (፪ኛጢሞ.፫፥፲፬)

መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ፡- ዘሪ ዘሩን ሊዘራ ወጣ፤ አንዱም ዘር በመንገድ ላይ ወደቀና ተረገጠ፣ ሌላውም በጭንጫ መሬት ላይ ወደቀ፤ በበቀለም ጊዜ ወዲያው ደረቀ፤ ሌላውም በእሾህ መካከል ወደቀ፣ በአደገም ጊዜ እሾሁ አነቀውና ደረቀ፡፡ “በመልካም መሬት ላይ የወደቀ ዘርም ነበረ፡፡ በበቀለም ጊዜ መቶ እጥፍ አፈራ” ይለናል፡፡ በተሰማራንበት ሁሉ መሬት የተባለውን የሰዎችን ልብ አለምልመን ዘር የተባለውን የእግዚአብሔርን ቃል የምንዘራ የወንጌል ገበሬዎች ሆነን መገኘት ይጠበቅብናል፡፡ (ሉቃ. ፰፥፬-፰)፡፡

በግቢ ጉባኤያት ሳለን መንፈሳዊውን ዕውቀት ለመገብየት እንሮጥ እንደነበረው ሁሉ ዕውቀትን ከእምነት ጋር አዋሕደን ወደ ዓለም ስንሰማራ ከቀደመው ይልቅ መትጋት፣ ለገባነውም ቃል ታማኞች ሆነን መገኘት ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ሕይወታችንን በቃለ እግዚአብሔር በማነጽ በተሰማራንበት ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባሏት መዋቅሮች ውስጥ ገብተን ቃለ እግዚአብሔርን መማርና ማስተማርን የሥራችን አንድ አካል ልናደርግ ይገባል፡፡

ጌታችን በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ወንጌል “ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ያጠፋታል፤ ሰውነቱን ስለ እኔና ስለ ወንጌል የሚያጠፋትም ያገኛታል፡፡ ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ነፍሱን ግን ቢያጠፋ ለሰው ምን ይጠቅመዋል?” በማለት እንደገለጸው በተሰማራንበት ሁሉ ከፊታችን የሚያጋጥሙንን ፈተናዎች ሁሉ በመቋቋም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሰጠችን አደራ ታምነን ነፍሳችንን ማዳን፤ ለሌሎችም ብርሃን ሆነን የእግዚአብሔር መንግሥት ወራሾች እንሆን ዘንድ ዘወትር መትጋት ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ወብዙኃን ይትፌሥሑ በልደቱ፤ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” (ሉቃ. ፩፥፲፬)

መ/ር እንዳልካቸው ንዋይ

ይህን ቃል የተናገረው የእግዚአብሔር መልአክ ለካህኑ ዘካርያስ ነው፡፡ የጻፈልንም ከአራቱ ወንጌላውያን አንዱ የሆነው ቅዱስ ሉቃስ ነው፡፡ ይህ ቃል የተነገረለትም የካህኑ ዘካርያስና የኤልሳቤጥ ልጅ የሆነው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ነው፡፡ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አባቱ ዘካርያስ እናቱ ኤልሳቤጥ ይባላሉ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን እስኪወልዱ ድረስ በመካንነት (ያለ ልጅ) ኖረዋል፡፡

ጻድቃን መካን ሆነው የሚቆዩበት ጊዜ አለ፤ ኃጥአን መክነው የሚቀሩበት ሁኔታ አለ፡፡ እግዚአብሔር ባወቀ መክነው የሚቀሩም አሉ፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተገለጠው ምክነት (ልጅ መውለድ አለመቻል) በሦስት ዋና ዋና ምክንያቶች ሊመጣ ይችላል፡፡

. በኃጢአት፡

የሰው ልጅ ሕገ እግዚአብሔርን ሲተላለፍ፣ እግዚአብሔርን በሕይወቱ ማክበር ሲያቅተው፣ የቅዱሳንንም ክብር አልጠብቅ ሲል እግዚአብሔር ከቸርነቱ ብዛት የተነሣ ለሰው የሚሰጠውን ጸጋ ይነሳዋል፡፡ “ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታዎች ናቸው”ና፡፡ (መዝ.፻፳፯፥፫)  ልጅ ጸጋ ስጦታ ወይም ሀብት ነው፡፡ ጸጋ የሚሰጠው ደግሞ ለሚገባው ነው፡፡ ኃጢአት ደግሞ ጸጋን ያሳጣል፡፡ በኃጢአት ምክንያትም እግዚአብሔር ማሕፀናቸውን የዘጋባቸው እና ያለ ልጅ ያስቀራቸው ሰዎች አሉ፡፡ ከእነዚህም ሰዎች አንዷ የእስራኤል የመጀመሪያው ንጉሥ የሳዖል ልጅ እና በኋላም የነቢየ እግዚአብሔር የዳዊት ሚስት የሆነቸው ሜልኮል ናት፡፡

ዳዊት ታቦተ ጽዮን ከምርኮ በምትመለስበት ጊዜ ለታቦተ ጽዮን በዘመረ ጊዜ ሚስቱ ናቀችው፤ በዚህ ምክንያት እግዚአብሔር የሜልኮልን ማሕፀን ዘጋ፡፡ “ኢወለደት ሜልኮል እስከ አመ ሞተት፤ ሜልኮል እስከ ሞተችበት ቀን ድረስ ልጅ አልወለደችም፡፡” (፪ኛሳሙ. ፮፥፳፫) በማለት ይገልጻታል፡፡ በኃጢአት ከሚመጣው ምክነት ለመዳን ንስሓ መግባትና ወደ ፈሪሃ እግዚአብሔር መመለስ ይገባል፡፡

. ለሰዎች ጥቅም፡-

እግዚአብሔር የማይጠቅም ጸጋ አይሰጥም (፩ኛቆሮ. ፲፪፥፯) የቅዱሱ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት እናት እግዚእ ኃረያ እግዚአብሔርን ልጅ እንዲሰጣት በለመነችው ጊዜ አንድ ቃል ተናግራ ነበር፡፡ “የምትሰጠኝ ልጅ አንተን የሚፈራ የሚያገለግል ሰውን የሚያፍር ሃይማኖቱን የሚያከብር ይሁንልኝ ካልሆነ ግን ማህፀኔን ዝጋው” በማለት ነበር የተማጸነችው፡፡ (ገድለ ተ/ሃይማኖት፤ ገጽ ፳፰፤ ምዕ. ፰፥፶-፶፫) እግዚአብሔርም ጸሎቷን ሰምቶ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን የመሰለ ልጅ ሰጥቷታል፡፡ የማይጠቅም ልጅ ቢሆን ግን እግዚአብሔር አይሰጥም፡፡

. የሚወለደው ልጅ የተለየ ቅዱስ ከሆነ፡-

እግዚአብሔር ስለሚሰጠን ልዩ ስጦታ ብሎ ስጦታውን ሊያዘገየው ይችላል፤ ይህም የሚሆንበት ምክንያት ውድ ስጦታ ስለሆነ በደጅ ጥናት፣ በጸሎት፣ በሱባኤ እንዲሆን ሁለተኛም አክብረን እንድንይዘው ነው፡፡ በዚህ ምክንያት በቅዱሳት መጻሕፍት እንደተነገረው ስለሚሰጣቸው በጎ ስጦታ በምክነት ያቆያቸው ቅዱሳን ሰዎች አሉ፡፡

ለምሳሌ፡-  ሣራ የአብርሃም ሚስት ለ፺ ዓመት ያህል በምክነት የቆየችው ይስሐቅን የመሰለ በጎ ስጦታ እግዚአብሔር ስላዘጋጀላት ነው፡፡ ሐና እና ኢያቄምም ያለ ልጅ የቆዩት የአምላክ እናት የምትሆን ድንግል ማርያምን ሊሰጣቸው ስለሆነ ነው፡፡ ዛሬም በዓለ ልደቱን የምናከብርለት ቅዱስ ዮሐንስ ወላጆቹ በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ የሚሄዱ ጻድቃን ሲሆኑ ያለ ልጅ በምክነት የቆዩት ክርስቶስን በዮርዳኖስ ባሕር ለማጥመቅ የሚበቃውን ደግ ሰው ስለሚወልዱ ነበር፡፡

ለዚህም ነበር መልአኩ የቅዱሱን ልደት አስመልክቶ “በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ሲል የተናገረው፡፡ ልደቱ ከእናትና አባቱ ጀምሮ የክርስቶስን መምጣት ለሚጠባበቁ ሁሉ ደስታ ነበር፤ ለዚህም ነው መልአኩ ስሙ ዮሐንስ ይባላል ያለው፡፡ ዮሐንስ ማለትም ፍስሓ ወሐሴት ፍቅር ወሰላም ማለት ነው፡፡ ከፅንሰቱ ጀምሮ እስከ ልደቱ በመላ ሕይወቱም ሁለንተናው በተአምር የተመላ ልጅ በማግኘታቸው ወላጆቹ ደስታን አግኝተዋል፡፡ ሲፀነስ የአባቱ አንደበት የመልአኩን ቃል ባለመቀበሉ ሲዘጋ ሲወለድ ደግሞ የአባቱን አንደበት ከፍቶ ቤቱን በደስታ የመላ ቅዱስ ሕፃን ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ዮሐንስን ልደት በየዓመቱ በታላቅ ክብር ታከብረዋለች፡፡

በዚህ አንጻር የእኛ ልደት እንዴት ነው እየተከበረ ያለው? በእኛ ልደት ቤተሰቦቻችን፣ ቤተ ክርስቲያንና ሀገራችን ምን ተጠቀሙ? በየዓመቱስ ልደታችን የምናከብርበት መንገድ ኦርቶዶክሳዊ የቅዱሳንን መንገድ የተከተለ ነው? የሚለውን ጥያቄ ራሳችንን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በልደቱ ብዙዎች ደስ ተሰኝተዋል፡፡ ምክንያቱም በትምህርቱ በተአምራቱ ብዙዎች ተጠቅመዋልና “የጌታን መንገድ አዘጋጁ” እያለ በትምህርቱ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ ያቀርብ ነበር፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በውኃ ለንስሓ በዮርዳኖስ ባሕር እያጠመቀ ለአማናዊ ጥምቀት ሰዎችን ያዘጋጅ ነበርና ብዙዎች በመወለዱ ተጠቅመዋል፡፡ እኛስ በመወለዳችን ማን ተጠቀመ? በቅዱስ ዮሐንስ መወለድ ግን ብዙ ድንቆች ሆነዋልና ደስ ይለናል፡፡ አስቀድመን እንዳነሣነው ስለ ክርስቶስ እያስተማረ፣ በበረሐ በመኖሩና ጌታን በማጥመቁ ቅድስናውን ማድነቅ፣ በቃል ኪዳኑም መጠቀም ከእኛ ይጠበቃል፡፡

ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ይህን ሲያስረዳ እንዲህ አለ።-

ሰባኬ ወንጌል በጥዑም ልሳኑ፣

ርስነ መለኮት ገሠሠት የማኑ፣

ፀጕረ ገመል ተከድነ ዘባኑ፣

ለዮሐንስ ሂሩቶ ንዜኑ ንዜኑ፡፡

ትርጉሙም

በጣፋጭ አንደበቱ ወንጌልን የሚሰብክ፤ የሚያቃጥል መለኮትን የዳሰሰች ቀን እጅ፤ ጀርባው በግመል ፀጕር የተሸፈነ የዮሐንስን ደግነት ፈጽመን እንናገራለን በማለት አመስግኖታል፡፡

በአጠቃላይ የዮሐንስ ልደት ለብዙዎች ደስታ ነው የተባለው ሰውን ሁሉ በንስሓ ወደ ጌታው የሚመልስ በመሆኑ ነው፡፡ ስለሆነም እኛም መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የጌታ መንገድ ጠራጊ ነውና በልደቱ ደስ ሊለን ይገባል፡፡

አምላከ ዮሐንስ ይርዳን፣ በበረከተ ልደቱም ይባርከን፡፡

“እነሆም ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካአል ሊረዳኝ መጣ” (ዳን. ፲፥፲፫)

ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ “መኑ ከመ አምላክ፤ ማን እንደ እግዚአብሔር” ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ወንጌላዊው ቅደስ ዮሐንስ በራእዩ “በእግዚአብሔር ፊት የቆሙ ሰባት መላእክትን አየሁ” ብሎ ከተናገረላቸው መላእክት ውስጥ አንዱ ሲሆን፤ የሰባቱም ሊቃነ መላእክት አለቃ እንዲሆን እግዚአብሔር መርጦ ሹሞታል፡፡

እስራኤላውያን ለ፪፻፲፭ ዓመታት በግብፃውያን ከደረሰባቸው የባርነትና የሥቃይ ዘመናት በኋላ በሊቀ ነቢያት ሙሴ አማካይነት ወደ ምድረ ርስት ሲወጡ ቀን በደመና፣ ሌሊቱን በብርሃን እየመራ ማድረሱን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በማለት ይነግረናል፡- “በመንገድ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀሁልህም ስፍራ ያገባህ ዘንድ እነሆ፥ እኔ መልአኬን በፊትህ እልካለሁ። ራስህን ጠብቅ፣ ስማው፣ እምቢም አትበለው፤ ስሜም በእርሱ ስለሆነ ይቅር አይልምና፡፡” (ዘጸ. ፳፫፥፳-፳፩) እንዲል፡፡

ቅዱስ ሚካኤል ከግብሩ በመነሣት በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ በልዩ ልዩ ቅጽል ስያሜዎች ይጠራል፡፡ ከእነዚህም መካከል “መጋቤ ብሉይ፣ መልአከ ኃይል፣ እንዲሁም መልአከ ምክር” ይባላል፡፡ መጋቤ ብሉይ መባሉ በብሉይ ኪዳን ከእግዚአብሔር እየተላከ እስራኤላያንን ቀን በደመና፣ ሌሊቱን በብርሃን እየመራ መና ከሰማይ እያወረደ በመመገቡ፣ መልአከ ኃይል መባሉም እግዚአብሔር በእርሱ አማካይነት ታላላቅ ሥራዎችን በመሥራት ኃይሉን የገለጸ፣ ዲያብሎስን ከነሠራዊቱ ድል ያደረገ በመሆኑ ሲሆን፣ መልአከ ምክር ወይም የእግዚአብሔር የምክሩ አበጋዝ የተባለበት ምክንያት እግዚአብሔርን በምክሩ ይረዳዋል ለማለት ሳይሆን እግዚአብሔር የሚሠራውን ሥራ ለወዳጁ ለቅዱስ ሚካኤል ይገልጽለታል፤ በእርሱም አማካኝነት ይሠራል ለማለት ነው፡፡

የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በስሙ ለሚማጸኑ ሁሉ ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ከሚደርስባቸው ችግር ሁሉ የሚታደግ መልአከ ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት ቅዱስ ሚካኤል ያደረጋቸውን ቁጥር ስፍር የሌላቸው ተአምራት ቢኖሩም በተለይም በሰኔ ፲፪ ቀን ያደረገውን ተአምራት ከብዙ በጥቂቱ እንደሚከተለው በአጭሩ እንመለከታለን፡፡

በእስክንድርያ ሀገር አክላወባጥራ የተባለች ንግሥት የንጉሥ በጥሊሞስ ልጅ ዙሐል በሚባል ኮከብ ስም ያሠራችው ታላቅ ምኵራብ ነበረና በየዓመቱ ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን በዚያ ምኵራብ ሕዝቡ ተሰብስቦ ታላቅ በዓል ያደርጉ ነበር፡፡ በዚያም ምኵራብ ውስጥ ዙሐል የሚሉት ታላቅ የነሐስ ጣዖት ነበረና በዓሉ በሚከበርበት ዕለት ብዙ ፍሪዳዎችን ያርዱለት ነበር፡፡ ሊቀ ጳጳሱ እለእስክንድሮስ እስከተሾመበት ዘመን ድረስ ለዚያ ጣዖት እንዲህ ሲያደርጉ ኖሩ፡፡

እለእስክንድሮስ በእስክንድርያ ከተማ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ እና ቆስጠንጢኖስም በነገሠ ጊዜ የክርስትና ሃይማኖት ስለ ተስፋፋች ያን ጣዖት አባ እለእስክንድሮስ ሊሠብረው ወደደ፡፡ ነገር ግን የሀገሩ ሰዎች “እኛ በዚህ ቦታ ይህን በዓል ማክበርን ለምደናል፡፡ እነሆ ከአንተ በፊት ዐሥራ ስምንት ሊቃነ ጳጳሳት አልፈዋል፤ ይህን ልማዳችንንም አልለወጡብንም” በማለት ተከራከሩት፡፡ አባ እለእስክንድሮስ ግን ገሠፃቸው፤ አስተማራቸውም፡፡

“ይህ ጣዖት የማይጎዳና የማይጠቅም ነው፡፡ እርሱንም የሚያመልክ ሰይጣናትን ያመልካቸዋል፡፡ምክሬንስ ብትሰሙ ቀድሞ እንደ ነበረ አድርጌ ይህን በዓል እሠራላችኋለሁ፤ ይኸውም ጣዖቱን እንድንሰብረው፣ ምኵራቡንም እንድንባርከውና በከበረ መልአክ በመላእክት አለቃ በሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አድርገን እንድንሰይመው ነው፡፡ እኛም ይህን ታላቅ በዓል እንሠራለን፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነት ያለው ስለ ኾነ ስለ እኛ ይማልዳልና፡፡” ይህንንም ብሎ በዚህ በጎ ምክር አስወደዳቸው፤ እነርሱም ታዘዙለት፡፡

ከዚህም በኋላ ያንን ምኵራብ አድሰው በዚህ የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ስም ቤተ ክርስቲያን አደረጉት፡፡ በዚችም ዕለት አከበሩዋት፡፡

እግዚአብሔርን የሚፈራ የከበረ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ በየወሩ በዐሥራ ሁለተኛው ቀን ይልቁንም በሰኔ እና በኅዳር ወር አብልጦ የሚያከብር አንድ ሰው ነበር፡፡ በጐረቤቱም ርኅራኄ የሌለው አንድ ባለ ጠጋ ሰው ነበረ፡፡ ይህን እግዚአብሔርን የሚፈራውን ሰው የከበረ መልአክ የሚካኤልን በዓል በሚያደርግበት ጊዜ ይጠላውና ያቃልለው ነበር፡፡ ከኃላፊው ዓለም ድካምም የሚያርፍበት ጊዜ በደረሰ ጊዜ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ታደርግ ዘንድ ሚስቱን አዘዛት፡፡ ከዚህም በኋላ ዐረፈ፡፡

ሚስቱም ፀንሳ ነበር፡፡ የመውለጃዋ ደርሶ ምጥ በያዛት ጊዜም በታላቅ ጭንቀት ውስጥ ሆና ጸለየች፡-የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ሚካኤልን በአማለጅነቱ ይደርስላት ዘንድ ተማጸነቸው፡፡ በዚህ ጊዜ በቤቷ ውስጥ ብርሃን በራ፡፡ መልኩ ውብ የኾነ ወንድ ልጅንም ወለደች፡፡ የእግዚአብሔርም መልእክተኛ ቅዱስ ሚካኤል ከሰማይ ወርዶ ሕፃኑን እንዲህ ብሎ ባረከው፡- “ርኅራኄ የሌለውን የዚህን ባለጠጋ ገንዘብና ሀብት፣ ጥሪቱንም ዅሉ ይህ ሕፃን እንዲወርስ እግዚአብሔር አዝዟል” አለ፡፡

ባለ ጠጋውም በቤቱ፣ በዐልጋው ላይ ሳለ ጌታ ጆሮውን ከፍቶለት ይህን ነገር ከመልአኩ ሰማ፡፡ ይህንን በሰማ ጊዜ ታላቅ ኀዘን ደረሰበት፡፡ ሕፃኑንም የሚገድልበትን ምክንያት ይፈልግ ጀመረ፡፡   ምክንያትም አዘጋጅቶ “የሚያገለግለኝ ልጅ ይኾነኝ ዘንድ ልጅሽን ስጪኝ፡፡ እኔም እየመገብኹና እያለበስኹ አሳድገዋለሁ፡፡ ለአንቺም ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሻለሁ” አላት፡፡ ይህንንም ነገር ከባለጠጋው በሰማች ጊዜ ስለ ችግሯ እጅግ ደስ አላት፡፡ ልጅዋንም ሰጠችው፡፡

ባለጠጋውም በልጁ ቁመት ልክ ሣጥን አሠርቶ ሕፃኑን በሣጥኑ ውስጥ አስገብቶ ከዘጋበት በኋላ   ወስደው በባሕር ጣሉት፡፡ ለሃያ አንድ ቀናትም ሳጥኑ በባሕሩ ላይ እየተንሳፈፈ ወደ አንድ ወደብ ደረሰ፡፡ በዚያም በጎቹን አሰማርቶ የሚጠብቅ አንድ ሰው ነበርና ሣጥኑን በውኃ ላይ ተንሳፎ አየው፡፡ እርሱም ከባሕሩ አውጥቶ ወደ ቤቱ ወሰደው፡፡ ሳጥኑ በቁልፍ የተቆለፈ ስለነበር ለመክፈት ተቸገረ፡፡ ነገር ግን አንድ አሣ የሚያጠምድ ሰው በማግኘቱ “መረብህን በኔ ስም ጣል፡፡ ለሚያዘው ዓሣ ዋጋውን እሰጥሃለሁ አለው፡፡

አጥማጁም እንዳለው አደረገ፡፡ ያን ጊዜም ታላቅ ዓሣ ተያዘ፡፡ ይዞም ወደ ቤቱ ሔደ፡፡ ለራትም ይጠብሰው ዘንድ አረደው፡፡ በሆዱም ውስጥ መክፈቻ አገኘ፡፡ በሣጥኑ ቀዳዳም በአስገባው ጊዜ ፈጥኖ ተከፈተ፡፡ በውስጡም ታናሽ ብላቴና አገኘ፡፡ ልጅ የለውም ነበርና ታላቅ ደስታ ደስ አለው፡፡ ጌታችንንም አመሰገነው፡፡ ሕፃኑንም በመልካም አስተዳደግ አሳደገው፡፡ ሕፃኑም አድጎ ጐልማሳ ኾነ፡፡

ከብዙ ዘመናትም በኋላ ያ ባለ ጠጋ ተነሥቶ ወደዚያ አገር ሔደ፡፡ በመሸም ጊዜ ወደ በግ ጠባቂው ደጅ ደረሰ፡፡ በግ ጠባቂውን “እስከ ነገ የምናድርበት ማደሪያ በአንተ ዘንድ እናገኛለን?  ኪራዩንም እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ባለ ጠጋውም በዚያ አደረ፡፡ ራት በሚቀርብም ጊዜ ከባሕር ላገኘው ልጅ “ባሕራን” ብሎ ሲጠራው ባለ ጠጋውም ሰምቶ “ልጅህ ነውን?” ብሎ ጠየቀው፡፡ በግ ጠባቂውም “አዎ፤ ታናሽ ሕፃን ኾኖ ሳለ ከሃያ ዓመት በፊት ከባሕር ላይ አግኝቼዋለሁና እግዚአብሔር የሰጠኝ ልጄ ነው” አለው፡፡

ባለጠጋውም እርሱ ወደ ባሕር የጣለው ሕፃን መኾኑን ዐውቆ እጅግ አዘነ፡፡ በማግሥቱም ጎዳናውን ሊጓዝ በተነሣ ጊዜ ሰይጣናዊ ምክንያት አመካኝቶ በግ ጠባቂውን እንዲህ አለው፡- “ከአገር ስወጣ በቤቴ የረሳሁት ጉዳይ ስላለ እንድልከው ልጅህን ትሰጠኝ ዘንድ እሻለሁ፡፡ እኔም የድካም  ዋጋውን ሃያ ወቄት ወርቅ እሰጥሃለሁ” አለው፡፡

የብላቴናውም አባት ስለ ገንዘቡ ደስ ብሎት ልጁ ባሕራንን ሰጠው፡፡ ባለ ጠጋው ወደ መጋቢው ደብዳቤ ጻፈ፤ “ይቺን ደብዳቤ በምታነባት ጊዜ ደብዳቤዋን ይዞ የመጣውን ልጅ ገድለህ በጉድጓድ ውስጥ ጣለው፤ ማንም ዐይወቅ፡፡” በማለት በመካከላቸውም የሚተዋወቁበትን ምልክት ጽፎ አሸጋት፤ ለባሕራንም ሰጠው፡፡

ባሕራንም ሲጓዝም ሰንብቶ የአንዲት ቀን ጉዞ ሲቀረው እነሆ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል በንጉሥ ጭፍራ አምሳል በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ “አንተ ጐልማሳ የያዝኸው ምንድነው?” አለው፡፡ “ከአንድ ባለጠጋ የተጻፈች መልእክት ናት” አለው፡፡ “ያቺን ደብዳቤ አሳየኝ አለው፡፡ እርሱም ስለ ፈራ ሰጠው፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ያቺን የሞት መልእክት ደመሰሳት፡፡ በእርሷ ፈንታም በንፍሐት ለውጦ እንደህ ብሎ ጻፈ፤ “ይቺን ደብዳቤ ይዞ ለመጣ ባሕራን ለሚባል ሰው ልጄን አጋቡት፡፡ በውስጥና በውጭ ያለ ንብረቴንና ጥሪቴን፣ ወንዶችና ሴቶች ባሮቼን፣ ጠቅላላ ንብረቴንም አውርሼዋለሁና የፈለገውንም ሊያደርግ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና እኔን አትጠብቁኝ፡፡ እኔ ብዙ እዘገያለሁ ለዚህም በእኔና በአንተ መካከል ይቺ ምልክት እነኋት፡፡” በማለት ደብዳቤውን አሽጐ ለባሕራን ሰጠው፡፡ “ወደ ባለጠጋው ቤት ሒደህ ይቺን ደብዳቤ ለሹሙ ስጠው፡፡በጎዳናም እኔ እንደ ተገናኘሁህ    አትንገረው፡፡ እንዳይገድልህም ይህን የሞት ደብዳቤ ለውጬልሃለሁ” አለው፡፡ ባሕራንም “እሺ ጌታዬ ያዘዝኸኝን ዅሉ አደርጋለሁ” አለ፡፡

ባሕራንም ወደ ባለ ጠጋው ቤት በደረሰ ጊዜ ያቺን ደብዳቤ ለሹሙ ሰጠው፡፡ በአነበባት ጊዜ በመካከላቸው ያለውን ምልክት አገኘ፡፡ አስተውሎም እርግጠኛ እንደ ኾነ ዐወቀ፡፡ ከዚህም በኋላ ለባሕራን ሠርግ አዘጋጅቶ እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል የባለ ጠጋውን ልጅ አጋቡት፡፡ ዐርባ ቀን ያህልም ደስታና ሐሴት እያደረጉ ኖሩ፡፡ ከዚህ በኋላ ባለ ጠጋው ከሔደበት መመለሻው ጊዜ ኾኖ በደስታ የኾነውን የመሰንቆና የእንዚራ ድምፅ ሰምቶ “ይህ የምሰማው ምንድነው”  ብሎ ጠየቀ፡፡ እነርሱም “ስሙ ባሕራን ለተባለ የአንተን ደብዳቤ ላመጣ ጐልማሳ ሰው ልጅህ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ እነሆ ለዐርባ ቀናት በሠርግ ላይ ነው፡፡ገንዘብህንና ጥሪትህን ዅሉ ወንዶችና ሴቶች ባሮችህን አንተ እንዳዘዝኽ ሰጥተውታል” አሉት፡፡ ይህንም በሰማ ጊዜ ደንግጦ ከፈረሱ ላይ ወደቀ በድንገትም ሞተ፡፡

ባሕራንም በጎ ሥራዎችን የሚሠራ ኾነ፡፡ የተገለጠለትና ከመገደል ያዳነው የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሚካኤል እንደ ኾነ፤ ሊገድለው የሚሻውን የባለ ጠጋውን ጥሪቱን ዅሉ ያወረሰውም እርሱ እንደ ኾነ ተረዳ፡፡ የዚህንም የከበረ መልአክ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን መታሰቢያ በየወሩ ያደርግ ጀመረ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠራለት፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕሉን አሥሎ በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ አደረገው፡፡ ከእርሱም ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡

ዳግመኛም በዚህች ቀን እግዚአብሔርን የሚፈራ አስተራኒቆስ የሚስቱ የቅድስት አፎምያ የዕረፍቷ መታሰቢያ ኾነ፡፡ ይህም ሰው በየወሩ ሦስት በዓላቶችን እያከበረ ኖረ፡፡ እሊህም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የልደቱ መታሰቢያ በየወሩ በሃያ ዘጠኝ፤ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በዓል መታሰቢያ በየወሩ በሃያ አንድ፤ የከበረ የመላእክት አለቃ የኾነ የቅዱስ ሚካኤል በዓል መታሰቢያም በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን ናቸው፡፡ የሚሞትበትም ጊዜው ሲቀርብ እርሱ ሲሠራው የነበረውን ምጽዋት ይልቁንም እሊህን ሦስቱን በዓላት እንዳታስታጉል ሚስቱን ቅድስት አፎምያን አዘዛት፡፡

እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባሏን ለመነችው፡፡ እርሱም አሠርቶ ሰጣትና በቤቷ ውስጥ በክብር አኖረችው፡፡ ባሏም ከዐረፈ በኋላ ባሏ ያዘዛትን መሥራት ጀመረ፡፡ ሰይጣን ግን ቀናባት፡፡ በመበለት ሴት መነኵሲት ተመስሎ ከእርሷ ጋር ተነጋገረ፡፡ እንዲህም አላት፤ “እኔ አዝንልሻለሁ፤ እራራልሻለሁም፡፡ ገንዘብሽ ሳያልቅ፣ የልጅነትሽም ወራት ሳያልፍ አግብተሽ ልጅ ትወልጂ ዘንድ እመክርሻለሁ፡፡ባልሽም መንግሥተ ሰማያትን ወርሷል፡፡ ምጽዋትም አይሻም፡፡” አፎምያም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ “እኔ ከሌላ ሰው ጋራ ላልገናኝ በእግዚአብሔር ፊት ቃል ኪዳን አድርጌያለሁ፡፡ ርግቦችና መንጢጦች እንኳ ሌላ ባል አያውቁም፡፡ በእግዚአብሔር አርአያ ከተፈጠሩ ሰዎች ይህሊኾን እንዴት ይገባል?”

ምክሩንም ባልሰማች ጊዜ አርአያውን ለውጦ በላይዋ ጮኸባት፡፡ እንዲህም አላት፤ “እኔ በሌላ ጊዜ እመጣለሁ፡፡” እርሷም የከበረ የመልአኩ የሚካኤልን ሥዕል ይዛ አሳደደችው፡፡ ከዚህም በኋላ ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን የከበረ የመልአኩ የሚካኤል በዓል በሚከብርበት ዕለት እርሷም የበዓሉን ዝግጅት ስታዘጋጅ ሳለች ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ “አፎምያ ሆይ! ሰላም ላንቺ ይኹን! እኔ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ነኝ፡፡ ጌታ ወደ አንቺ ልኮኛልና እርሱም ይህን መመጽወትሽን ትተሽ ለአንድ ምእመን ሚስት ትኾኚ ዘንድ አዞሻል፡፡” ባል የሌላት ሴት መልሕቅ የሌለውን መርከብ እንደምትመስል ዕወቂ፤ እንደ አብርሃምና ያዕቆብ እንደ ዳዊትም እንደነርሱ ያሉ ብዙ ሴቶችን እንዳገባ፤ እግዚአብሔርንም ደስ እንዳሰኙት ከብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ጥቅሶችን ያመጣላት ጀመረ፡፡

ቅድስትአፎምያም መልሳ “አንተ የእግዚአብሔር መልአክ ከኾንኽ የመስቀል ምልክት ከአንተ ጋር ወዴት አለ? የንጉሥ ጭፍራ የኾነ ዅሉ የንጉሡን ማኅተም ሳይዝ ወደ ሌላ ቦታ አይሔድምና” አለችው፡፡ ሰይጣኑም ይህንን በሰማ ጊዜ መልኩ ተለወጠና አነቃት፡፡ እርሷም ወደ ከበረው መልአክ ወደ ሚካኤል ጮኸች፡፡ ወዲያውኑም ደርሶ አዳናት፡፡ ያንም ሰይጣን ይዞ ይቀጣው ጀመረ፡፡ ሰይጣኑም ጮኸ፡፡ “ማረኝ፤ ያለ ጊዜዬ አታጥፋኝ፤ እግዚአብሔር እስከ ዓለም ፍጻሜ ታግሦናልና” እያለ ለመነው፡፡ ከዚያም ተወውና አባረረው፡፡

የከበረ መልአክ ሚካኤልም እንዲህ አላት፤ “ብፅዕት አፎምያ ሆይ! ሒደሽ የቤትሽን ሥራ አዘጋጂ፡፡አንቺ ዛሬ ከዚህ ዓለም በሞት ትለዪአለሸና፡፡ እነሆ እግዚአብሔርም ዐይን ያላየውን፣ ጆሮም ያልሰማውን፣ በሰው ልብም ያልታሰበውን አዘጋጅቶልሻል፡፡” ይህንንም ብሎ ሰላምታ ሰጣት፡፡ ወደ ሰማያትም ዐረገ፡፡ የበዓሉንም ዝግጅት እንደሚገባ ከፈጸመች በኋለ ወደ ኤጲስቆጶሱና ወደ ካህናቱ ዅሉ ላከች፡፡ ወደ እርሷም በመጡ ጊዜ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ይሰጧቸው ዘንድ ገንዘቧን ዅሉ አስረከበቻቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ተነሥታ ጸለየች፡፡ የከበረ የመልአኩ የቅዱስ ሚካኤልንም ሥዕል አንሥታ ታቅፋ ሳመችው፡፡ ያን ጊዜም በሰላም ዐረፈች፡፡

ስለዚህም የዚህን ታላቅ የከበረ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ለማድረግመታገል ይገባናል፡፡ “እነሆም ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካአል ሊረዳኝ መጣ” (ዳን. ፲፥፲፫) እንዲል ቅዱስ ሚካኤል በምልጃው ይራዳን ዘንድ ልንማጸነው ይገባል፡፡ እርሱ ከሰይጣን ወጥመድ ያድነን ዘንድ በዘመናችን ዅሉም ይጠብቀን ዘንድ፤ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይ ዘንድ፤ መከራችንንም ያርቅ ዘንድ፤ የምድራችንንም ፍሬ ይባርክ ዘንድ፤ ፈቃዱንም ለመሥራት ይረዳን ዘንድ፤ ከእኛ ወገን የሞቱትን ዕረፍተ ነፍስ ይሰጥ ዘንድ፤ ወደ መንገድ የሔዱ አባቶቻችንና ወንድሞቻተንን ወደ ቤቶቻቸው በሰላም፣ በጤና ይመልሳቸው ዘንድ፤ በመካከላችንም ፍቅር ያደርግልን ዘንድ፤ እስከ መጨረሻዪቱም ሕቅታ ድረስ በቀናች ሃይማኖት ያጸናን ዘንድ፤ የክርስቶስ ወገኖች የኾኑ መኳንንቶቻችንንም ጠብቆ በወንበሮቻቸው ላይ ያጸናቸው ዘንድ፤ የሳቱትንም ወደ ቀናች ሃይማኖቱ ይመልሳቸው ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ ይለምናልና፡፡

የቅዱስ ሚካኤል አማላጅነትና ጥበቃው አይለየን፡፡ አሜን፡፡

 

ምንጭ፡– መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፲፪ ቀን፡፡

“እየባረካቸው ራቃቸው” (ሉቃ. ፳፬፥፶፩)

ዘመነ ዕርገት ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በኋላ ከ፵ኛው ቀን ጀምሮ እስከ ጰራቅሊጦስ ድረስ ያለው ነው፡፡ ዕርገት ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከ፱ኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ነው፡፡ የጌታችን ዕርገት ታሪክ በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፬፥፶ ጀምሮ የተጻፈ ሲሆን ደቀ መዛሙርቱ በዓይናቸው እያዩት፣ እየባረካቸው ከዓይናቸው መሠወሩ ተገልጧል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገቱን ለሐዋርያት ማሳየቱ ለቅዱሳን፣ ጻድቃን ዕርገት እንዳላቸው ለማሳየት ነው፡፡ እርሱ ሰው ሲሆን ያየው የለም፤ሲያርግ ግን ሁሉ እያየው ነው፡፡ በዚህ ዓለም ላይ ፴፫ ዓመት ከሦስት ወር እየተመላለሰ ክርስትናን ሰብኳል፣ ድውያንን ፈውሷል፤ ከተነሣ በኋላም ለ፵ ቀናትም ለሐዋርያት እየተገለጠ ጸሎተ ኪዳንን አስተምሮ ዐርጓል፡፡

ይህም ማለት ፶፻ወ፭፻ (አምስት ሺህ አምስት መቶ) ዘመን ሲፈጸም በዘመነ ማቴዎስ ማክሰኞ መንፈቀ ሌሊት ተወልዶ በዘመነ ማርቆስ በዕለተ ሐሙስ በ፫ ሰዓት ግንቦት ፰ ቀን ዐረገ፡፡

ጌታችን ከትንሣኤ በኋላ ዐርባ ቀን ሐዋርያትን እያስተማረ ስለሚመጣው አጽናኝ እያስረዳ ሰነበተ (ዮሐ. ፳፩፥፫) ቅዱስ ዳዊትም “እግዚአብሔር  በመለከት ድምፅ  ዐረገ ዘምሩ ለአምላካችን ዘምሩ ለንጉሣችን ዘምሩ፣ እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና በማስተዋል ዘምሩ”   ይላል (መዝ.፵፮፥፭—፯)

ሠለስቱ ምዕትም “ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ፤ በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ” ብለዋል፡፡ (ጸሎተ ሃይማኖት) “እንግዲህ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን ሹ በላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም ሞታችኋልና ሕይወታችሁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሮአልና፡፡ ሕይወታችሁም የሆነ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ በዚያን ጊዜ እናንተ ደግሞ   ከእርሱ ጋር ትገለጣላችሁ” እንዲል፡፡ (ቆላ. መ፫፥፩-፬)

የዕርገት በረከቶች

. ቡራኬ፡- “እጆቹን በላያቸው ላይ ጭኖ ባረካቸው፣እየባረካቸውም ራቃቸው ወደ ሰማይም ዐረገ” ይላል፡፡ (ሉቃ. ፳፬፥፶፩) ይህ ቡራኬ ለቅዱሳን ሐዋርያት በመዋዕለ ሥጋዌው ከሆነው የመጨረሻ ቡራኬ ነው፡፡ ይህን ቡራኬ ለመቀበል መጽናትና መታገስ ይጠይቃል፡፡ በክርስቶስ ትምህርት የጸኑት የተባረኩበት ነው፡፡ቡራኬው ዛሬም የማይቋረጥ መሆኑን ሲያረጋግጥልን ደግሞ “እየባረካቸው ራቃቸው፣ ወደ ሰማይም ወጣ” በማለት ይነግረናል፡፡

ዛሬም ቤተ ክርስቲያናችን በቅዳሴ ፍጻሜ ላይ ካህኑ እጆቹን አመሳቅሎ “እግዚአብሔር ከሁላችሁ ጋር ይሁን” በማለት የዕርገት በረከት (ቡራኬ) ለምእመናን ስታድለው(ስታካፍለው) ትኖራለች፡፡ ይህ ደግሞ “እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” (ማቴ. ፳፰፥፳) በማለት የገባልን ኪዳን ማረጋገጫ ቡራኬ ነው፡፡

፪. ሹመት፡- “ወእምዝ አውፅኦሙ አፍአ እስከ ቢታንያ ወአንሥአ እዴሁ ላዕሌሆሙ ወባረኮሙ፤ ወደ አፍአ እስከ ቢታንያ ድረስ አውጥቶ በአንብሮተ እድ እስከ ፖትርያርክነት ያለውን ማዕርግ ሾማቸው፤ ሾሟቸውም የርቀት ያይደለ የርኅቀት ተሰውሯቸው ወደ ሰማይ ዐረገ” (የሉቃስ ወንጌል አንድምታ ምዕራፍ ፳፬፥፶-፶፩)፡፡ በቅዱሳን ሐዋርያት እስከ ዕርገት ድረስ የተሰጣቸው ሹመት ሁሉ በቡራኬ የተረጋገጠው በዕርገት ዕለት ነው፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሥልጣን ሰጣቸው የሚለውን ሲያብራሩ አስቀድሞ የሰጣቸውን ለማጽናት ነው ብለው ያስተምራሉ፡፡

. ተስፋ፡-  መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት እንደሚወርድላቸው ተጽፏል፡፡ (ዮሐ. ፲፭፥፳፮፣ ሉቃ. ፳፬፥፵፱) ዳግመኛም ሐዋርያትን “እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ” (ዮሐ. ፲፬፥፫) በማለት የሰጠን የመጨረሻ ተስፋ የተረጋገጠበት ነው፡፡

“…. ወደሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት እንዲሁ ይመጣል” (የሐዋ. ፩፥፲፩) በማለት አስረግጠው ቅዱሳን መላእክት ተናግረዋል፡፡ አቡቀለምሲስ ዮሐንስም “እነሆ ከደመና ጋር ይመጣል፣ ዐይንም ሁሉ የወጉትም ያዩታል” (የዮሐንስ ራዕይ ፩፥፯) በማለት በዕርገቱ ያየነውን ደመና በዳግም ምጽአቱ እንደምናየው አስተምሮናል፡፡

                 ወስብሐት ለእግዚአብሔር