“ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ”(ኢዩ.፪፥፲፫)

በእንዳለ ደምስስ

ይህንን ቃል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በነቢዩ ኢዩኤል ላይ አድሮ ልባቸው ለደነደነና ኃጢአት በመሥራት ለሚተጉት አይሁድ የተናገረው ተግሣጽ ነው፡፡ እግዚአብሔር በባሕርይው ታጋሽ፣ ሁሉን ቻይ ሲሆን ስለ በደላቸው ብዛት ማጥፋት ሲችል ይመለሱ ዘንድ ከመካከላቸው ነቢያትን እያስነሣ ሲገስጻቸው እንመለከታለን፡፡ ስለ ኃጢአታቸው ተጸጸተው  ወደ እርሱ ለሚጮኹ፣ ልብሳቸውን ሳይሆን ልባቸውን ለሚቀዱ ራሳቸውን ለአምላካቸው አሳልፈው ለሚሠጡ ደግሞ ምሕረቱ ቅርብ ነውና በዘመኑ ነቢየ እግዚአብሔር ኢዩኤልን አስነስቶ “አሁንስ ይላል አምላከችሁ እግዚአብሔር፣ በፍጹም ልባችሁ በጾም፣ በልቅሶና  በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ፡፡ ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ አምላካችሁም እግዚአብሔር በሓሪና ይቅር ባይ፣ ቁጣው የዘገየ ምሕረቱም የበዛ ለክፋትም የተጸጸተ ነውና ወደ እርሱ ተመለሱ” እያለ ሰብኳቸዋል፡፡(ኢዩ.፪፥፲፪)፡፡

ሕዝቡም ልባቸው የደነደነ፣ ለጽድቅ የዘገዩ ቢሆኑም ነቢዩ ኢዩኤል ከእግዚአብሔር የታዘዘውን ከመናገር ወደ ኋላ አላለም፡፡ የእግዚአብሔርን ምሕረትና ቸርነትን ዘንግተው ራሳቸውን ለዓለም አሳልፈው በመስጠት ለኃጢአት በመንበርከካቸው ፈጣሪያቸውን አሳዘኑ፡፡ እግዚአብሔር ግን በየዘመናቱ ወደ እርሱ የቀረቡትንና የተመረጡትን ሰዎችን እያስነሳ ከሚመጣው መቅሰፍት ሕዝቡ ያመልጡ ዘንድ፣ ምድሪቱም ከበደላቸው ታርፍ ዘንድ ነቢዩን ልኮላቸዋል፡፡ “በጽዮን መለከትን ንፉ፣ ጾምንም ቀድሱ፣ ምሕላንም ዐውጁ፣ ሕዝቡንም ሰብስቡ፣ ማኅበሩንም ቀድሱ፣ ሽማግሌዎችንም ጥሩ፣ ጡት የሚጠቡትንና ሕፃናትን ሰብስቡ፣ ሙሽራው ከእልፍኙ ሙሽራይቱም ከጫጉላዋ ይውጡ” እያለ ወደ እግዚአብሔር እንዲጮኹ ነግሯቸዋል፡፡ (ኢዩ.፪፥፲፫)፡፡ እግዚአብሔርም ሕዝቡ በፍጹም ልባቸው መጸጸታቸውንና በነቢዩ ተግሣጽ ልባቸውን ወደ እርሱ እንደመለሱ በተመለከተ ጊዜ ስለ ሕዝቡ ራርቷል፤ ምሕረቱንም በምድሪቱ ላይ አፍስሷል፡፡

በሊቀ ነቢያት ሙሴ ዘመንም እግዚአብሔር ሕዝቤ ያላቸው እስራኤላውያን በግብፅ ምድር በባርነት ሲሰቃዩ ከኖሩበት ዐራት መቶ ሠላሳ ዘመን በኋላ በግብፃውያን ላይ ዐሥር ተአምራትን ከፈጸመ በኋላ፣ በዐሥራ አንደኛው ባሕረ ኤርትራን ከፍሎ አሻግሯቸዋል፡፡ እስራኤላውያን “ሕዝቤ” እያለ ይጠራቸው የነበሩት ፈጣሪያቸውን ረስተው በበደል ረክሰው በተመለከተ ጊዜ ሙሴን እያመለከተ ቁጣው በነደደ ጊዜ “ሕዝብህ” እያለ ጠርቷቸዋል፡፡ “እግዚአብሔር ሙሴን ተናገረው እንዲህም አለው፡- ‘ከግብፅ ምድር ያወጣኻቸው ሕዝብህ በድለዋልና ሂድ፣ ፈጥነህ ውረድ፡፡ ካዘዝኋቸው መንገድ ፈጥነው ፈቀቅ አሉ”(ዘጸ.፴፪፥፯) እንዲል፡፡

ከሥነ ፍጥረት ጀምሮ ብንመረምር የሰው ልጆች ያልበደሉበት ጊዜ የለም፣ ነገር ግን እግዚአብሔር ቁጣውን በትዕግሥት፣ ሕዝቡን በንስሓ እየመለሰ የመጣውን መቅሰፍት አሳልፎ የምሕረት እጆቹን ዘርግቶ ተቀብሏቸዋል፡፡ “የእግዚአብሔርም አገልጋዮች ካህናት በወለሉና በምስዋዑ መካከል እያለቀሱ ‘አቤቱ ለሕዝብህ ራራ፤ አሕዛብም ይገዙአቸው ዘንድ ርስትህን ለማላገጫ አሳልፈህ አትስጥ፣ ከአሕዛብም መካከል አምላካቸው ወዴት ነው? ስለምን ይላሉ’ ይበሉ፡፡ እግዚአብሔርም ስለ ምድሩ ቀና፤ ለሕዝቡም ራራለት” በማለት እግዚአብሔር ፍጹም መሐሪና ቸር እንደሆነ ይነግረናል፡፡ (ኢዩ.፪፥፲፯-፲፰)፡፡ ሕዝቡንና ምድሪቱን በምሕረት ጎብኝቷልና፡፡

የነነዌ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት ክፋትን አደረጉ፣ የእግዚአብሔርም ቁጣ ነደደ፣ ነገር ግን ለፈጠረውና የእጁ ሥራ ለሆነው ለሰው ልጅ እግዚአብሔር ይራራልና ነቢዩ ዮናስን አስነሳላቸው፡፡ ነቢዩ ዮናስ የነነዌ ሰዎችን ልበ ደንዳናነት፣ ጽድቅን ከመሥራት ራሳቸውን ያራቁና ለዓለም ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡ መሆናቸውን ያውቃልና “የእግዚአብሔር ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል መጣ፡- “ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የክፋታቸውም ጩኸት ወደ ፊቴ ወጥቷልና ለእነርሱ ስበክ” የሚለውን ቃል ሲሰማ፡፡ ነገር ግን ዮናስ የታዘዘውን ማድረግ አልፈለገም፡፡(ዮና.፩፥፩-፪)፡፡ ለራሱ ክብር ተጨንቋልና፣ ዞሬ ብሰብክም አይሰሙኝም ይህን ከማይ ሐሰተኛ እንዳልባል በሚል ከእግዚአብሔር ፊት መኮብለልን ምርጫው አደረገ፡፡ ካለበት ተነሥቶም ወደ ተርሴስ በመርከብ ይጓዝ ዘንድ ወደደ፡፡ ቅዱስ ዳዊት “ወደ ሰማይ ብወጣ አንተ በዚያ አለህ፤ ወደ ጥልቁም ብወርድ አንተ በዚያ አለህ” እንዲል (መዝ.፻፴፱፥፰)፡፡ እግዚአብሔር በሁሉ የመላ መሆኑን ዘንግቶ መኮብለልን መረጠ፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ሸሽቶ ማመለጥ የሚችል የለምና በዓሣ አንበሪ ሆድ ውስጥ ለሦስት ቀንና መዓልት አሳርፎት ወደ ነነዌ እንደወሰደው መጽሐፍ ይነግረናል፡፡ እግዚአብሔር ቃሉ አይታጠፍም፣ ላያደርገው አይናገርምና በነነዌ ምድር ስላሉት ንጹሐን ስለሆኑት ሕፃናትና እንስሳት እንዲሁም ምድሪቱ ይራራልና የታዘዘውን ይፈጽም ዘንድ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፣ የነገርኩህንም የመጀመሪያውን ስብከት ስበክላት” አለው፡፡ ነቢዩ ዮናስ በዚህ ወቅት ነው ከእግዚአብሔር ሸሽቶ ማምለጥ እንደማይቻል የተረዳው፡፡ ምርጫ አልነበረውምና ወደ ነነዌ ምድር ሄዶ የታዘዘውን ፈጸመ፡፡ ሕዝቡም በዮናስ ስብከት አማካይነት ለሦስት ቀናት ጾሙ፣ ጸለዩ፣ ንስሓም ገቡ፡፡ ቸር የሆነው እግዚአብሔር ስለ ሕዝቡ ኃጢአት ሊመጣ ያለውን ጥፋት ወደ ምሕረት ለውጦታል፡፡

ዛሬ በሀገራችን ከነነዌ ሰዎች የባሰ ኃጢአት ነግሶ ወንድም በወንድሙ ተጨካክኖ ሲገዳደል ማየት እየተለመደ መጥቷል፡፡ ትላንት በታሪክ እንዲሁም በመጽሐፍ ቅዱስ እንዳነበብነው በገሐድ ሞት፣ ስደትና መከራ በኢትዮጵያ ምድር ላይ ሲፈጸም እያየን ነው፡፡ ኃጢአታችን ከሰዶምና ገሞራ ከፍቶ በአደባባይ ኃጢአትን መሥራት እንደ ነውር መቆጠር የቀረ እስኪመስል ድረስ ቆሽሸናል፡፡ የነነዌ ክርስቲያኖችን በአኒዩ ዮናስ አድሮ እንደገሰጻቸው እኛንም የሚገስጽ፣ ወደ ትክክለኛው መንገድ የሚመራን ያስፈልገናል፡፡ እኛም ወደ ጽድቅ ጎዳና ልናመራ፣ ክፍውንም ልንጠየፍ፣ ኃጢአትንም ከመሥራት ልንቆጠብ ያስፈልጋል፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ኢዩኤል “ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ” እንዲል በተሰበረ ልብ ወደ እግዚአብሔር እንመለስ፣ ጽድቅንም እንከተል፡፡ ለቅደስት ቤተ ክርስቲያናችን ሰላምን፣ ለሕዝቡም ፍቅር አንድነትን ያድልልን፡፡ አሜን፡፡

“በወንድማማችነትም ፍቅርን ጨምሩ” (፪ኛጴጥ.፩፥፯)

በቀሲስ ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

ክፍል ሦስት

ፍቅር የሁሉ ማሰሪያ ነው፡” የሺህ ፍልጥ ማሰሪያው ልጥ” “እንደሚባለው የምግባራት ሁሉ መደምደሚያ  ፍቅር ነው፡፡ ስለዚህ በወንድማማችነት ፍቅር መጨመር እንደሚገባ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ አስገንዝቦናል፡፡ “እርስ በርሳችሁ ከመዋደድ በቀር ለማንም   ዕዳ አይኑርባችሁ ባልንጀራውን የወደደ ግን ሕግን ሁሉ ፈጸመ” (ሮሜ.፲፫፥፰) ብሏልና፡፡ የሕግ ሁሉ ፍጻሜው ፍቅር ነው፡፡ እሱም በሁለት መልኩ ይፈጸማል የመጀመሪያው ሕግ እግዚአብሔር አምላካችንን በፍጹም ልባችን፣ በፍጹም አሳባችን፣ በፍጹም ኃይላችን መውደድ ሲሆን ሁለተኛውም ባልጀራችንን እንደ ራሳችን አድርገን መውደድ ነው፡፡

በመሆኑም  እነዚህ  ከላይ  ጀምሮ የዘረዘርናቸው ሁሉ  በእኛ  ቢሆኑ  መንፈሳዊ  ፍሬን ማፍራት እንደሚቻለን ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ እንዲህ አስገንዝቦናል፡፡ ይህም ወጣትነት መንፈሳዊ ፍሬዎቻችን ጎልተው የሚታዩበት ተግተን ለአገልግሎት የምንሰማራበትን ሰፊ አገልግሎትን የምንፈጽምበት ስለሆነ ከፊት ይልቅ መትጋት ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡

ወጣትነት በእግዚአብሔር ቃል ካልበለጸገ  ከውስጥ በሚመነጭ ፈቃደ ሥጋ ምክንያት ጥያቄ ውስጥ የሚከት ፈታኝ ወቅት ነው፡፡ ውጫዊውን ነገር ሁሉንም ለመጨበጥ የራስ ተነሣሽነት ሲያይል፣ ውስጣዊው ፈቃድ ደግሞ ዐይን ያየውን ልብ የተመኘውን ለመፈጸም በሚነሣሳበት ጊዜ የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደሆነ ፈትነን ከክፉ ምግባራት የምንርቅበትን የእግዚአብሔርን መንገድ ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡ ይህን ለማድረግም የሚያስችሉን መንፈሳዊ ትጥቆችን መያዝ አስፈላጊ ነው፡፡ እነሱም በመንፈሳዊ ሕይወት ጠንካራ የሚያደርጉንና ፍቅረ እግዚአብሔርን የሚጨምሩልን ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት ሲሆኑ ቅዱሳት ገዳማትን መሳለምና የቅዱሳንን ታሪክ እንዲሁም የኑሮ ፍሬ መመልከት ወሳኝ ነው፡፡

ለዚህም ነው ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ “በነፍሳችሁ ዝላችሁ እንዳትደክሙ ከኃጢአተኞች በደረሰበት እንዲህ ባለ መቃወም የጸናውን እስኪ አስቡ” (ዕብ.፲፪፥፫)  በማለት ያስተማረን፡፡

ስለዚህ በኑሮአችን መንፈሳዊ ፍሬ ማፍራት እንዲቻለን የቀድሞ ስንፍና ካለብን እሱን እየተውን በትጋት መንፈሳዊ ሩጫችንን ልንፈጽም ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሁሉንም በትጋት እንደ ፈጸመ ሲያስረዳን “መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ ሩጫዬንም ጨርሻለሁ ሃይማኖቴንም ጠብቄአለሁ እንግዲህስ የጽድቅ አክሊል  ይቆየኛል ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው እግዚአብሔር በዚያ ቀን ለእኔ ያስረክባል ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም” (፪ኛጢሞ.፬፥፯) ብሏል፡፡

ያለንበት ዘመን መንፈሳዊ ሕይወታችንን፣ አገልግሎታችንን ብሎም እምነታችንን የሚፈታተን መሆኑ ይታወቃል፡፡ ለዚህ ደግሞ የመጀመሪያ ተፈታኝ ወጣቱ ክፍል እንደሆነ የማይካድ  ሐቅ ነው፡፡ ወቅቱ ለመንፈሳዊ ሕይወት ፈተና የሚሆን ዓለማዊነት (secularism) በዘመናዊነትና  በሥልጣኔ ሰበብ  ተስፋፍቶ ትውልዱ ፈጣሪው እግዚአብሔርን እየተወ በሙት ፍልስፍና እየተመካ ወደ ጥፋት እየሄደ መሆኑ ላስተዋለው ሁሉ ግልጽ ነው፡፡ ይህም ዓለም  ወደ አንድ መንደር (globalization) የመጣችበት፣ ቴክኖሎጂው እጅግ የመጠቀበት ወቅት ስለሆነ ሩቅ መሔድ ሳይጠበቅብን ባለንበት ሥፍራ ሆነን ዓለምን ስንቃኝ የባህል መወራረሶች እንዳሉ ልብ ይሏል፡፡ እነዚህ የየሀገራቱ ባህሎች ደግሞ የራሳቸውን ተጽእኖ በሃይማኖታችንና በሥነ ምግባራችን ላይ ያሳድራሉ፡፡

ሀገራችን  ኢትዮጵያ  የብዙ  ባህሎች፣  ቋንቋዎችና  ማኅበረሰቦች  ባለቤት  እንደሆነች ይታወቃል፡፡ በቀደሙት አባቶቻችን ሃይማኖታዊ ሆነ ባህላዊ ጥንካሬዎች ያላትን ሀብት ጠብቃ ያስቆየች ሀገር ናት፡፡ እስከ አሁንም ድረስ የራሷ ቋንቋ፣ የራሷ ፊደል፣ የራሷ ባህል ያላት  ስትሆን  ብዙዎች  ባህሎቻችን  ሃይማኖታዊ አንድምታ፣  ሃይማኖታዊ  ምልከታ፣ ሃይማኖታዊ ትውፊት፣ ሃይማኖታዊ ይዘት  አላቸው፡፡ በርግጥ  በሀገራችን ስለነበረውና ስላለው ባህል ስናነሣ ጠቃሚና ጎጂ ብለን በሁለት መልኩ ማየቱ አስፈላጊ ነው፡፡ ስለዚህ ጎጂ ባህሎችን እያስወገድን ጠቃሚ የሆኑ ባህሎችን፣ ትውፊቶችን ግን ልናስቀጥላቸው ይገባል፡፡

ነገር ግን ዓለም ወደ አንድ መንደር በመጣችበት በዚህ ዘመን ከላይ እንዳየነው በተለያዩ መገናኛ ብዙኀን በሚታዩት፣ በሚሰሙትና በሚለቀቁት ነገሮች ጆሮአችን ብዙ ነገሮችን ይሰማል፡፡ ዐይናችንም ጠቃሚም የሆኑ ወይም በተቃራኒው ደግሞ ለክርስቲያናዊ ሕይወታችን  ጎጂም  የሆኑ  ነገሮችን  ያያል፡፡ ስለዚህ  የራሳችንን  ጠቃሚ  ወጎችን ባህሎችን፣  ትውፊቶችን ሳንለቅ  በምዕራቡ  ዓለም  የሚታዩትን ልቅ  የሆኑ ተግባሮችንና እሳቤዎችን አለማስተናገድ ብልህነት ነው፡፡

እነዚህ ከውጪው ዓለም የምናያቸውና የምንሰማቸው ለሃይማኖታችንና ለበጎ ምግባራችን ጠቃሚ ለሆኑ ወጎቻችንና ትውፊቶቻችን ፀር ወይም ማደብዘዣ ብሎም ማጥፊያ የሆኑ በሥልጣኔ ስም ርኵሰትን የሚያስፋፉትን ፀረ ሃይማኖት ተግባራት ንቆና ተጸይፎ ማለፍ ከአሁኑ  ትውልድ  የሚጠበቅ  ጥበብ  ነው፡፡  በርግጥ  በውጪው  ዓለም  የሚታዩና የሚሰሙ ሁሉም ጎጂ ናቸው ወይም ለሃይማኖታችንና ለመንፈሳዊ ሕይወታችን እንቅፋት ናቸው ማለት አይደለም፡፡ ምክንያቱም ቴክኖሎጂው  ያፈራቸው፣ ሥልጣኔው ያስገኛቸው መልካም ነገርን በቀላሉ የምናስተላልፍባቸው፣ሃይማኖትን የምንሰብክባቸው፣መረጃ የምንለዋወጥባቸው በአጠቃላይ አገልግሎታችንን በቀላሉ የምንከውንባቸው ብዙ  ጠቃሚ ነገሮችም አሉ፡፡

ዓለም አሁን ለደረሰችበት የሥልጣኔ ማማ ቅርብ የሆነ ወጣቱ ትውልድ እነዚህን ጎጂና ጠቃሚ ምንጮችን በማስተዋል በጥልቀት ሊመረምራቸውና ሊያጤናቸው ይገባል፡፡ ምክንያቱም የአሁኑ ዘመን በልማድና በየዋህነት ብቻ የምንኖርበት አይደለም፡፡ ብዙ ምርምርንና ጥናትን ይጠይቃል፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ወደ ዓለም ሲገቡ እንዴት ሆኖ ማገልገልና መኖር እንዳለባቸው ሲመክር “እነሆ እኔ እንደ በጎች በተኩላዎች መካከል እልካችኋለሁ እንግዲህ እንደ እባብ ብልሆች እንደ ርግብም የዋሆች ሁኑ” (ማቴ.፲፥፲፮ ) ብሏቸዋል፡፡

ስለዚህ ከፊት ይልቅ ዘመኑ እየከፋ ስለመጣ ያውም የዓለሙ ፍጻሜ ስለደረሰ ምልክቶቹም እየተፈጸሙ ስለሆነ አብዝተን ልንጾም፣ ልንጸልይ፣ ልንሰግድ ያስፈልጋል፡፡ አሁን የምንተኛበት ጊዜ ሳይሆን የምንነሣበት፣ የምናቀላፋበት ጊዜ ሳይሆን የምንነቃበት ወቅት ነውና ከፊት ይልቅ መትጋት ተገቢ ነው፡፡ ይህ ዘመን እጅግ ፈታኝ ነውና እናስተውል፤ እንትጋ፡፡

                     እግዚአብሔር ለሁላችን ትጋቱን ማስተዋሉን ያድለን አሜን፡፡

“ጾም ትፌውስ ቁስላ ለነፍስ” (ጾመ ድጓ)

ጾም ሥጋ ለነባቢት ነፍስ ትገዛ ዘንድ የተሠራ ሕግ ነው፡፡ ልዑለ ባሕርይ ቅዱስ እግዚአብሔር በጥንተ ልደት ሰውን /አዳምን/ እንዲህ ብሎ አዘዘው፡፡ “ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፣ ነገር ግን መልካሙንና ክፉውን ከምታስታውቀው ዛፍ አትብላ፡፡ ከእርሱ በበላህ ቀን የሞት ሞትን ትሞታለህና፡፡” (ዘፍ.፪፤፲፮) ሲል የጾምን ሕግ ሲያስተምረው እናያለን፡፡ ከዐራቱ ባሕርያተ ሥጋና ከሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ የተፈጠረው ሰው ለራሱ ሁለት ባሕርያት አሉት፡፡ እነዚህም ባሕርይ እንስሳዊና ባሕርይ መልአካዊ ይባላሉ፡፡

ባሕርይ እንስሳዊ ልብላ፣ ልጠጣ፣ ልደሰት፣ ይድላኝ ይላል፡፡ “ቀዳሜ ሕይወቱ ለሰብእ እክል ወማይ፣ አስቀድሞ የሰው ሕይወቱ እህልና ውኃ ነው፡፡” እንዲል መጽሐፈ ሲራክ፡፡ ዳዊትም “እክል ያጸንዕ ኃይለ ሰብእ፣ እህል የሰውን ኃይል ያጸናል” ይላልና፡፡ ባሕርይ መልአካዊ ደግሞ ልጹም፣ ልጸልይ፣ ልስገድ፣ ልመጽውት ይላል፡፡ “ዓይነ ኵሉ ነፍስ ይሴፎ ኪያከ፣ የሁሉ ሰውነት ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል” እንዲል (መዝ.፻፵፬፤፲፭)፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጻውሎስም “በነገር ሁሉ፣ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ፡፡” (ፊል.፬፤፮) በማለት አበክሮ ያስገንዝባል፡፡ እንግዲህ የእግዚአብሔርን አገልግሎት በሚገባ ማከናወን የሚቻለው በጸሎት በመትጋት፣ በመጾም፣ በመስገድና ንጽሕናን በመጠበቅ እንደሆነ ከአበው የሕይወት ልምድ እንረዳለን፡፡

ጾም በኃጢአት ጦር ተወግታ ለቆሰለች ነፍስ ዓይነተኛ ፈውስ መሆኑና ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ተመልሶ ከፈጣሪ ጋር ለመታረቅ የሚያስችል መሣሪያ መሆኑን በትንቢተ ኢዩኤል ተጽፎ እናገኛለን፡፡ እንዲህ ሲል ”አሁንስ ይላል እግዚአብሔር በፍጹም ልባችሁ በጾም፣ በልቅሶ፣ በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ” ይለናል፡፡ (ኢዩ.፪፤፲፪)፡፡ ሥጋ ደካማ ነው በምኞት ወጥመድ ይጠመዳል፣ በዚህ ዓለም ፍትወት ተተብትቦ ይወድቃል፡፡ ነገር ግን የሥጋን ምቾትና ፍላጎት በመግታት ለምግብና ለመጠጥ ምርኮኛ ከመሆን ርቀንና ተለይተን ሥጋችንን የምንቀጣበት መሣሪያ ጾም ነው፡፡ የመልካም ሥነ ምግባርም መፍለቂያ ምንጭ ነው፡፡

በመጽሐፈ መነኮሳት “ጾም ለጸሎት እናቷ፣ ለአርምሞ እህቷ፣ ለእንባ መፍለቂያው፣ ለበጎ ሥራ ሁሉ ጥንተ መሠረት ናት፡፡” ይላል፡፡ ስለዚህ ጾም ከጽሉላት ምግብ ብቻ የምንታቀብበት ብቻ ሳይሆን በጠቅላላው ሕዋሳተ ሥጋችንን የምንገታበት ልጓም ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ጾመ ድጓ በተባለው የዜማ ድርሰቱ ላይ ይህንኑ ሲገልጽ እንዲህ ይላል፡- “ዓይን ክፉ ከማየት ይጹም፣ ልሣንም ክፉ ከመናገር ይጹም፣ ጆሮም ክፉ ከመስማት ይጹም ፍቅርንም በመያዝ” ይላል፡፡ ይህ ማለት በጾም ወራት በዓይናችን ቅዱሳት መጻሕፍትን እንድንመለከትበት፣ በአንደበታችን ቃለ እግዚአብሔርን እንድንናገርበት፣ በጆሮአችን መልካሙን ዜና ትምህርተ ወንጌል እንድናደምጥበት፣ ፍቅረ እግዚአብሔርና ፍቅረ ቢጽን ገንዘብ አድርገን በነፍስ በሥጋ እንደንጠቀምበት ያስገነዝበናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ጾም በመንፈሳዊ የሕይወት ጉዞአችን መሰናክል ከሚሆኑን ርኩሳን መናፍስትና ረቂቃን አጋንንት ጋር በምናደርግው ውጊያና ተጋድሎ ላይ ኃይል እንድናገኝና ከፈተና እንድንድን ይረዳናል፡፡

ጾም እግዚአብሔር የማይወደውን ሥራ እየሠሩ ቢጾሙት ወይም በሰው ዘንድ ጿሚ መስሎ ለመታየትና ውዳሴ ከንቱን በመሻት ቢጾሙት ቅጣትን ያመጣል፡፡ ነገር ግን ከቂም ርቆ፣ ፍቅርን ይዞ የሠሩትን በማወቅም ባለማወቅ የፈጸሙትን ኃጢአት እያሰቡ በመጸጸት በዐንብዓ ንስሐ እያዘኑ እየተከዙ ቢጾሙት ሰማያዊ ዋጋ ያሰጣል፣ የኃጢአት ሥርየትን ያስገኛል፡፡

ሀገር በወራሪ ጠላት በተከበበች ጊዜ በኃጢአት አባር፣ ቸነፈር፣ በሽታና ረሓብ በታዘዘ ጊዜ ሕዝቡ ራሳቸውን ዝቅ አድርገው በንስሐ ተመልሰው ስለ ችግራቸው ከእግዚአብሔር እርዳታን ምሕረትን፣ ይቅርታን በተማጸኑ ጊዜ ምዓቱን በምሕረቱ፣ ቁጣውን በትዕግሥቱ መልስ አስገኝቶላቸው ከመከራ ሥጋ ይድናሉ፡፡ ይህም የጸሎት፣ የጾምና የጸሎት ውጤት ነው፡፡ ምእመናንም ይህን የመሰለ የጾምን ጠቃሚ መሣሪያነት በመረዳት በጾሙ ወራት ቅዱስ ዳዊት ”ብፁዕ ዘይሌቡ ላዕለ ነዳይ ወምስኪን፤ ለችግረኛና ለምስኪን የሚያስብ ምስጉን ነው፡፡” (መዝ.፵፤፩) ያለውን በማሰብ ለተራቡ ከእንጀራ ቆርሶ፣ ለተጠሙት ከማይ ቀድቶ፣ ለታረዙት አልብሶ ሌባ ግንቡን አፍርሶ ግድግዳውን ምሶ ከማይወስዱበት ከሰማያዊው ቤት መዝገብን ማኖር ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም በዝናብ አብቅሎ፣ በፀሐይ አብስሎ ከሚመግብ ፈጣሪ ተስፋ በረከትን በመሻት መጾም ይገባል፡፡ ጾመን፣ ጸልየን በረከት እንድናገኝ አምላካችን እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ አሜን፡፡

“ታስበው ዘንድ ሰው ምንድን ነው?” (መዝ.፰፥፬)

ሊቀ ነቢያት ሙሴ እግዚአብሔር ሰውን በመልኩ እንደ ምሳሌው መፍጠሩን  ጽፎልናል (ዘፍ.፩፥፳፮)፡፡ ከሃያ ሁለቱ ሥነ ፍጥረታትም በእግዚአብሔር መልክ የተፈጠረ ሰው ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ክቡር ሆኖ የተፈጠረ ሰው በብዙ መንገድ እግዚአብሔርን ሲበድል ይታያል፡፡ ከመጀመሪያው ሰው አዳም ጀምሮ የሰው ድካሙንና በደሉን ስናይ እንደ ቅዱስ ዳዊት ሰው ምንድን ነው? እንላለን፡፡ ከዚያ በላይ ደግሞ እጅግ የሚያስደንቀው እንዲህ ለሚበድለው ሰው እግዚአብሔር የሚያደርገው ምሕረትና የሚሳየው ፍቅር ነው፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ስለ ሰው ክቡር ተፈጥሮ በመሰከረበት የዝማሬ ክፍል ‹‹ሰብእሰ እንዘ ክቡር ውእቱ ኢያእመረ ወኮነ ከመ እንስሳ ዘአልቦ ልብ ወተመሰሎሙ፤ ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አላወቀም ልብ እንደሌላቸው እንስሶችም ሆነ መሰላቸውም››(መዝ፵፰፥፲፪) በማለት  እግዚአብሔር ሰውን አክብሮ የፈጠረው መሆኑንና ሰው ግን ይህንን የከበረ ተፈጥሮውን ልብ እንደሌላቸው እንስሳት በመሆን እንዳጎሳቆለ ይገልጻል፡፡

አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ፍቅር ነውና በፍቅር ተስቦ በበደል ምክንያት ለተጎሳቆለው ሰው የገባለትን የምሕረት ቃል ኪዳን ለመፈጸም ሰው ሆነ፡፡ ለዘመናት በዲያብሎስ ቁራኝነት፣ በሲዖል ባርነት ተገዝቶ ይኖር ለነበርው ሰው ነጻነትን ሰበከለት፡፡ በኃጢአት ምክንያት ርስቱን አጥቶ ስደተኛ ወደ ሆነው ወደ ጎስቋላው ሰው መጣ፡፡ ታስረን ለነበርን መፈታትን፣ ባሮች ለነበርን ልጅነትን፣ ተቅበዝባዥ ለነበርን ዕረፍትን፣ ሙታን ለነበርን ሕይወትን አደለን፡፡ እርሱ መድኃኒት ነውና ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርቱ ፈወሰ፡፡ በሥጋው ደዌ ሥጋ፣ በነፍሱ በባርነት ቀንበር ተይዞ ይሰቃይ ለነበረ መጻጒዕ ለተባለ በሽተኛ ሰው ያደረገውን የማዳኑን ሥራ ስንመለከትና በኋላ ግን መጻጒዕ የመለሰለትን ምላሽ ስናስተውል አይ ሰው! ብለን ትዝብታችን እንደ ቅዱስ ዳዊት “ታስበው ዘንድ ሰው ምንድን ነው?” እንላለን፡፡

መጻጕዕ ማለት በሽተኛ ማለት ነው፡፡ እርሱም በደዌ ዳኛ ተይዞ የአልጋ ቁራኛ ኾኖ ለብዙ ዓመታት(፴፰ ዓመት) ይኖር የነበረ በሰው የተናቀና የተረሳ ሰው ነው፡፡ መጻጒዕ ምንም እንኳ ለብዙ ዓመታት በመታመሙ ምክንያት ሰውነቱ ከአልጋ ተጣብቆ ከሰውነት ጎዳና የወጣ፣ ሰዎችም የናቁትና የተጸየፉት ቢሆንም፤ ፍጥረቱን የማይንቅ፣ ሰውን የሚወድ፣  ሳይንቅ

የጠየቀው፣ አይቶ በቸልታ ያላለፈው፣ የሰውን ድካሙን  የሚረዳ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደተረከው በኢየሩሳሌም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ቋንቋ “ቤተ ሳይዳ” የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፡፡ አምስትም መመላለሻ ነበረባት፡፡ ቤተ ሳይዳ ማለት ቤተ ሣህል (የይቅርታ ቤት) ማለት ነው፡፡ አምስት መመላለሻ የሚለውን ትርጓሜ ወንጌል እርከን ወይም መደብ ይለዋል፡፡ በእርከኑ ወይም በመደቡ ብዙ ድውያን ይተኛሉ፡፡ ከእነሱም ውስጥ የታወሩ፣ አንካሶች፣ የሰለሉ፣ ልምሾ የኾኑ፣ የተድበለበሉ፣ በየእርከን እርከኖቹ ላይ ይተኛሉ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ውኃውን ለመቀደስ በየዓመቱ በሚወርድ ጊዜ ድምፁ እስኪያስተጋባ ድረስ ውኃው ይናወጣል፡፡ ድውያኑም በዚያ ሥፍራ ተኝተው የውኃውን መናወጥ ይጠባበቃሉ፡፡ ምክንያቱም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ውኃው ሲናወጥ ቀድሞ ወደ ውኃው የገባ አንድ ሰው ከደዌው ይፈወስ ነበርና፡፡

ፈውሱ በየጊዜው ከዓመት አንድ ጊዜ ይደረግ የነበረው የእግዚአብሔር ተአምራት በአባቶቻችን ጊዜ ነበር እንጂ አሁንማ የለም ብለው ድውያኑ ከማመን እንዳይዘገዩ ሲኾን፣ የድውያኑ መፈወስ አለመደጋገሙም (በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ መፈጸሙም) በኦሪት ፍጹም ድኅነት እንዳልተደረገ ለማጠየቅ ነው፡፡ በዚያም ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፡፡ ከአልጋው ላይ ተጣብቆ ይኖር ነበር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ወደዚያ ሰው ቀርቦ አየው፡፡ ጌታችን ክብር ይግባውና ተጨንቀን እያየ ዝም የማይለን፣ ስንቸገርም የሚረዳን ቸር አምላክ ነውና መጻጕዕ በደዌ ዳኛ፣ በአልጋ ቁራኛ ተይዞ ለብዙ ዓመታት እንደ ተሰቃየ፣ ደዌው እንደ ጸናበት መከራውም እንደ በረታበት አውቆ በርኅራኄ ቃል “ልትድን ትወዳለህን?” አለው፡፡ ፈቃዱን መጠየቁ ነው፡፡

አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ፍትሐዊ ነውና ለማዳን የእያንዳንዳችን ፈቃደኝነት ይጠይቃል እንጂ ሥልጣን ስላለው፣ ክንደ ብርቱና ሁሉን ማድረግ የሚቻለው ስለሆነ ብቻ ያለፈቃዳችን የሚገዛን አምላክ አይደለም፡፡ በእኛ ላይ የሚያደርገውን የማዳኑን ሥራ “ልትነጻ ትወዳለህን፣ ምን እንዳደርግልህ ትሻለህ?” በማለት ከጠየቀ በኋላ “እንደ እምነትህ ይኹንልህ፤ እንደ እምነትሽ ይሁንልሽ” እያለ በነጻነት እንድንመላለስ ነጻነታችን ያወጀልን የፍቅር አምላክ ነው፡፡  መጻጕዕንም “ልትድን ትወዳለህን?” ባለው  ጊዜ  እሱ  ግን  የሰጠው  ምላሽ  እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ “ጌታ ሆይ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያው ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም፤ ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል” ብሎ መለሰለት፡፡ መጻጕዕ ሰዎች እንደሸሹት፣ በታመመ ጊዜ እንደተጸየፉት፣ “እንዴት ዋልህ? እንዴት አደርህ?” የሚለው ሰው እንዳጣ፣ ወገን አልባ እንደ ሆነ እና ተስፋ እንደ ቆረጠ ለጌታችን ተናገረ፡፡

ጌታችን የልብን የሚያውቅ አምላክ ሲሆን “ልትድን ትወዳለህን?” ብሎ የጠየቀበት ምክንያት አላዋቂ ሥጋን እንደ ተዋሐደ ለማጠየቅ ነው፡፡ አልዓዛር በሞተ ጊዜ “መቃብሩን አሳዩኝ፣ ወዴት ነው የቀበራችሁት?” እንዳለው ሁሉ መጻጕዕም በምላሹ “ሰው የለኝም” ማለቱ ኢየሱስ ክርስቶስን ሲያየው የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ ነውና የውኃውን መናወጥ ተጠባብቆ ያወርደኛል ብሎ በማሰቡ ነው፡፡ እንዲሁም አምስት ገበያ ሰው ይከተለው ነበርና አንዱን ሰው ያዝልኛል ብሎ ነው፡፡

ብዙዎቻችን የሕይወታችን ዋልታ በሰው እጅና በሰው ርዳታ ያለ ይመስለናል፡፡ ሰዎች ካልረዱን፣ ካልደጎሙን፣ አይዟችሁ ካላሉን፣ ከጎናችን ካልሆኑና በሰዎች ካልታጀብን ነገር ሁሉ የማይሳካልን ይመስለናል፡፡ ለዚህም ነው በሰዎች ትከሻ ላይ እንወድቅና እነሱ ሲወድቁ አብረን የምንወድቀው፡፡ ሲጠፉም አብረን ለመጥፋት የምንዳረገው፡፡ እስኪ ከሚደክመው ከሰው ትከሻ፣ ከሚዝለው ከሰው  ክንድ  እንውረድና በማይዝለውና በማይደክመው በአምላክ ክንድ  ላይ እንደገፍ፡፡ እርሱ መታመኛ ነው፤ ያሳርፋል፣ የማይደክምም ብርቱ መደገፊያ ነውና፡፡

መጻጕዕ ሁሉ ነገሩ በሰዎች እጅ ላይ ነው ብሎ ስላሰበና የሰዎች ርዳታ ስለ ቀረበት ተስፋ ቆርጦ ነበር፡፡ የተማመነባቸው ሰዎችም ሲርቁት ሕይወቱ ጨልሞበት ነበርና  “ሰው የለኝም” አለ (ዮሐ.፭፥፯)፡፡ የተቸገረውን ለመርዳት፣ ድኃውን ባዕለ ጸጋ ለማድረግ፣ የተጨነቀችቱን ነፍስ ለማጽናናት አማካሪ የማይሻው አምላክ ግን ወዲያውኑ “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ” አለው፡፡ መጻጕዕም ወዲያውኑ ዳነ፡፡ አልጋውንም ተሸክሞ ሔደ፡፡ ቀነ ቀጠሮ ሳይሰጥ፣ መሻቱን ተመልክቶ በአምላካዊ ቃሉ ፈወሰው፡፡

በዮሐንስ ወንጌል ትርጓሜ እንደ ተገለጸው የእግዚአብሔር መልአክ የቀሳውስት፣ ውኃው የጥምቀት፣ አምስቱ እርከን የአምስቱ አዕማደ ምሥጢር፣ አምስቱ ድውያን የአምስቱ ፆታ ምእመናን ማለትም የአዕሩግ፣ ወራዙት፣ አንስት፣ ካህናት፣ መነኮሳት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ እነዚህንም ሰይጣን የሚዋጋበት ለእያንዳንዱ እንደየ ድካሙ ሊያጠቃው ይሞክራልና ያንን ድል

የሚነሱበትን ምሥጢር እንደሚያድላቸው ያጠይቃል፡፡ አዕሩግን በፍቅረ ንዋይ፣ ወራዙትን በዝሙት ጦር፣ አንስትን በትውዝፍት (የምንዝር ጌጥ)፣ ካህናትን በትዕቢት፣ መነኮሳትን በስስት ጦር ሰይጣን ይዋጋቸዋል፡፡ እነርሱም በጥምቀት ባገኙት ኃይል (የልጅነት ሥልጣን) ድል ያደርጉታልና የዚያ ምሳሌ ነው፡፡ ለመጻጕዕ መፈወስ የዘመድ ብዛት፣ የሰዎች ርዳታ አላስፈለገውም፡፡ በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተፈውሷል፡፡ ለዚህም ነው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት   በመዝሙሩ “ችግረኛውን   ከቀማኛው   እጅ፤   ረዳት   የሌለውንም   ምስኪን ያድነዋልና” (መዝ.፸፪፥፲፪) ሲል የተቀኘው፡፡ ጻድቁ ኢዮብም እንዲሁ “ረዳት(ኃይል) የሌለውን ምንኛ ረዳኸው” (ኢዮ.፳፮፥፪) በማለት የእግዚአብሔርን አዳኝነት መስክሯል፡፡

የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በሕይወቱ የደረሰለት ሰው እንዲህ ይባረካል፡፡ ስለዚህ ገንዘብ፣ ሥልጣን፣ ወገን፣ ረዳት የለኝም በማለት ተስፋ የቆረጥን ሰዎች እግዚአብሔር ከሰውም፣ ከሥልጣንም፣ ከገንዘብም በላይ ነውና እርሱን ተስፋ አድርገን ሁል  ጊዜ በስሙ መጽናናት እና የሚያስጨንቀንን ሁሉ በእርሱ ላይ መጣል እንደሚገባን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ የሚፈልጉህ ሁሉ በአንተ ደስ ይበላቸው፤ ሐሴትም ያድርጉ፡፡ ሁል ጊዜ ማዳንህን የሚወዱ ዘወትር እግዚአብሔር ታላቅ ይሁን ይበሉ”(መዝ.፵፥፲፮) እንዳለው ሁል ጊዜም በአምላካችን እግዚአብሔር ደስተኞች እንሁን፡፡

መጻጒዕ የተፈወሰው በሰንበት ቀን ነበርና   አይሁድ በዚህ ቀን አልጋህን ልትሸከም አይገባህም ሲሉ ተቃወሙት፡፡ እርሱ ግን በተደረገለት ነገር ደስ ቢለውም ከእነርሱ ይልቅ ለሱ መልካም ነገር ያደረገለትን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በተደረገለት ነገር ሁሉ ሙሉ ተጠያቂው እርሱ ነው እንጂ እኔ ታዝዤ ነው ለማለት “ያዳነኝ እርሱ አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለኝ” አላቸው፡፡ አይሁድም መልሰው አልጋህን ተሸክመህ ሂድ ያለህ ሰው ማነው ብለው ጠየቁት፡፡ እርሱ ግን የፈወሰው ማን እንደሆነ አላወቀም ነበር፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ታስበው ዘንድ ሰው ምንድን ነው? ብሎ እንደ ጠቀሰው የረዳውን፣ ያዳነውን፣ ሰው ቢረሳውም እንኳ ያልረሳውን፣ ሰው ቢንቀው እንኳ ያልናቀውን፣ ጎስቋላ ሕይወቱን የጎበኘውን ጌታ አለማወቁ፣ ለማወቅም አለመጠየቁ ሰው ምን ያህል ደካማ ፍጡር እንደሆነ የምንማርበት ነው፡፡

ሰው እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ከ፳፪ቱ ሥነ ፍጥረት እጅግ ውብና በእግዚአብሔር መልክ እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠረ ድንቅ ፍጡር ሆኖ ሳለ የፈጠረውን፣ ቢወድቅ ያነሣውን፣ ቢጠፋ የፈለገውን፣ ቢራቆት የጸጋ ልብስ ያለበሰውን፣ ቢጎሳቆል ያከበረውን፣ ቢሰደድ ወደ ርስቱ የመለሰውን እግዚአብሔርን አውቆ ሊገዛለት እንደ ፈቃዱም ሊኖር ይገባል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ክርስቲኖች በጻፈላቸው መልእክቱ እንደጠቀሰው

‹‹እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱ መጠን እንዲሁ እግዚአብሔር ይህን የማይገባውን ይሠሩ ዘንድ ሰነፍ አእምሮን ሰጣቸው››(ሮሜ.፩፥፳፰) ይላልና ለማይረባ (ሰነፍ) አእመሮ ተላልፎ ላለመሰጠት እግዚአብሔርን ማወቅ፣መፈለግና መከተል ያስፈልጋል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በቤተ መቅደስ ሳለ ያን ያዳነውን ሰው አገኘውና “እነሆ ድነሃል ግን ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ዳግመኛ እንዳትበድል፣ ተጠንቀቅ አለው” ያም ሰው ሄዶ ያዳነው ጌታችን ኢየሱስ እንደሆነ ለአይሁድ ነገራቸው፡፡

መጻጉዕ ምንም እንኳን በዚያች አልጋህን ተሸክመህ ሂድ በተባለበትና ከደዌው በተፈወሰበት ሰዓት ለዘመናት ሲጠባበቅ የነበረውን ድኅነት በአንዲት ቃል ያዳነውን አምላክ ቢያንስ ከተደረገለት ከእግዚአብሔር ቸርነት ተነሥቶ ለማወቅ አለመፈለጉ በደል ሆኖ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተ መቅደስ አግኝቶት እርሱ እንዳዳነው ከነገረው በኋላ እንኳን ስለ ተደረገለት አመስግኖ አዳኝነቱን መመስከር ሲገባው ሁለተኛ በደል ጭራሽ ለመክሰስ ተሰለፈ፡፡

አይሁድም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሰንበት ድውይ ፈውሷል፣ጎባጣ አቅንቷል፣እውር አብርቷል ለምጽ አንጽቷል፣ሙት አስነሥቷል፣ጉንድሽ ተርትሯል፣አጋንንትን ከሰው ልቡና አውጥቷል ስለዚህ  ሰንበትን ሽሯል በሚል ክፉ ሴራቸው ያሳድዱትና ሊገድሉትም ይሹ ነበር፡፡ ጌታችን   መድኃኒታችን   ኢየሱስ   ክርስቶስ   የተራቡትን   ትቂት   እንጀራ   አበርክቶ እያበላ፣የተጠሙትን እያጠጣ፣ የተጨነቁትን እያጽናና፣ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ድውያነ ነፍስን በትምህርቱ እየፈወሰ ድሃውን ስለ ድህነቱ ሳይንቅ፣ባዕለ ጸጋውን ስለ ሃብቱ ሳያፍር የሁሉን ልብ በአባታዊ ፍቅሩ አንኳኳ፡፡ ብዙዎች ግን ልባቸው በክፋት ስለ ሞላ ዲያብሎስ ልባቸውን ስላደነደነው መጽሐፍ እንዳለ ‹‹የገዛ ወገኖቹ አልተቀበሉትም›› በእርሱ አምነው ከመቀበል ይልቅ ላለመቀበልና ወንጀለኛ ነው ለማለት የውሸት ምክንያት ይፈልጉ ነበር፡፡

አይሁድ ጌታችንን ከጲላጦስ ፊት አቅርበው ካቀረቡበት ክስ መካከል ዋና ዋናዎቹ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ይላል፣ ቤተ መቅደሱን አፍርሼ በሦስት ቀን እሠራዋለሁ ብሏል፣ ሰንበትን ሽሯል የሚሉ ነበሩ፡፡ በሰንበት ድውያንን በመፈወስ ሰንበትን ሽሯል ብለው ላቀረቡት ክስ መስካሪ ሆኖ መጻጒዕ ቀረበ፡፡ በሰንበት የፈወሰኝ እሱ ነው በማለት ያዳነውን አምላክ እጁን አንሥቶ በጥፊ መታው፡፡

በምህረቱ የተፈወሰች እጅ የሕይወትን ራስ ጌታዋን ለመምታት ተዘረጋች፡፡ ‹‹ባጎረስኩ እጄን ተነከስኩ›› እንደሚባለው ያ ለዘመናት ሰውነቱ ከአልጋ ተጣብቆ፣ ከሰውነት ጎዳና ወጥቶ በጽኑዕ ደዌ ሲሰቃይ ነበረ በሽተኛ ተሸክማው የኖረችውን አልጋ እሱም በተራው እንዲሸከማት ዕድሉን የሰጠውን አምላክ  ወንጀለኛ ነው ብሎ ጻድቁን ለመክሰስና ለመመስከር ከከሳሾች ጋር መተባበር የልቡና መታወር ነው፡፡ ልቡናቸው ብሩህ የሆነላቸው ቅዱሳን ሐዋርያት ግን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለሙ የከፈለውን ዋጋ ቤዛነቱን ለመመስከር የኤሁድ ዛቻና ማስፈራሪያ አልገደባቸውም፡፡ያዩትን፣የሰሙትን፣የተደረገላቸውን በአጠቃላይ ለሰው ልጅ የተከፈለለትን ዋጋ ከመመስከር የተሳለ ሰይፍ ፣የሚንበለበል እሳት፣ግርፋትና ስቅላት ፣ስደትና እርዛት መጠማትና ረሃብ  አላስቀራቸውም፡፡ይልቁንስ  እውነትን  በመመስከራቸው  በሚገጥማቸው  መከራ  ደስ እያላቸው ምስክርነታቸውን ሰጡ እንጂ፡፡ ‹‹ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያው የነበረውንና በጆሮአችን የሰማነውን በዐይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውንም እጆቻችንም የዳሰሱትን እንነግራችኋለን››(፩ኛዮሐ.፩፥፩) እንዲል፡፡

መጻጉዕ ግን ስለተደረገለት ምህረት እየመሰከረ እግዚአብሔርን ማክበር ሲገባው ቀና ብሎ እንዲራመድ ከወደቀበት ያነሣውን ክርስቶስን ለመቃወም ደፈረ፡፡ ‹‹የበላበትን ወጪት ሰባሪ›› ማለት እንዲህ ነው፡፡ ጌታችን ክርስቶስ መጻጉዕን በቤተ መቅደስ እንዳገኘው ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ዳግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ ብሎት ነበር፡፡ እሱ ግን በበደል ላይ በደል ጨመረ፡፡ እግዚአብሔር ሰውን ከመፍጠሩ አስቀድሞ ውብ አድርጎ ቢሠራውም ከንቱ ነገርን እንደሚመስል ያውቅ ነበር፡፡ ነገር ግን ለቸርነቱ ወሰን ለምህረቱ ገደብ የሌለው አምላክ ነውና ሰውን በፍቅሩ ጥላ ሥር እንዲያርፍ አድርጎታል፡፡

ቀድሞውኑ ሰው አታድርግ የተባለውን በማድረግ የማይገባውን በመመኘት ፈጣሪውን የበደለ፣ ከጸጋ እግዚአብሔር የተራቆተ፣ከገነት የተሰደደ፣ከክብር ያነሰ ሆኖ ቢገኝም የጠፋውን ሊፈግና ሊያድን ጌታችን ክርስቶስ በዓለም ተገለጠ፡፡  ሰው ሕግ አፍራሽ ሆኖ ሳለ ሠራኤ ሕግ ክርስቶስ ሕግን ሁሉ ፈጸመ፡፡ በደለኛው አዳም ካሳ ተከፈለለት፡፡ የሰው ልጅ የሚወደድ ሥራ ሳይኖረው በፍጹም ፍቅሩ ወደደውና ወደ ቀድሞ ርስቱ መለሰው፡፡ በዚህ ሁሉ የወደደን አምላካችን ልዑል እገዚአብሔር ከፍጹም ፍቅሩ የተነሣ ነውና ምሕረቱን ከእኛ ያላራቀብን ምስጋና ይድረሰው፡፡

“የክርስቶስ መስቀል ከተቀበረበት ስለ መውጣቱ”

በቀሲስ ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን የተሰቀለበት ቅዱስ መስቀል በአይሁድ ክፋት ተቀብሮ ለሦስት መቶ አመታት ያህል ቆሻሻ እየተደፋበት ኖረ፡፡ በዚህ የአይሁድ የክፋት ሥራ በኢየሩሳሌም የነበሩ ክርስቲያኖች በነገሩ እያዘኑ ቢኖሩም ከተቀበረበት ለማውጣት ግን አቅም አልነበራቸውም፡፡ ነገር ግን ከተቀበረበት ለማውጣት የሚያስችል መብትም ሆነ ሥልጣን ባያገኙም የተቀበረበትን ሥፍራ ግን ለይተው ያውቁት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ እስራኤልን ከሮም ቅኝ አገዛዝ ነጻ ለማውጣት ከስድሳ ስድስት(፷፮)  እስከ ሰብአ (፸) ዓ.ም ባደረጉት እንቅስቃሴ ጥጦስ የተባለው የሮም ንጉሥ ዘምቶ ኢየሩሳሌምን በሰብኣ(፸) ዓ.ም ደመሰሳት፡፡ ትልቁን የአይሁድ ቤተ መቅደስንም አቃጠለው፡፡ እስራኤላውያንም በመላው ዓለም ተበተኑ፡፡

ከዚህ በኋላ ክርስቲያኖች የተቀበረውን ቅዱስ መስቀል አስፈልገው ለማውጣት ቀርቶ በሃይማታቸውም ነጻነት ሊኖራቸው አልቻለም፡፡ ስለ ክርስትናቸውም ተሰዳጆች ሆኑ፡፡ በዚህም ምክንያት ቅዱስ መስቀሉ ለአይሁድ ያለ ማንም ከልካይ ለሦስት መቶ ዓመት ያህል የቆሻሻ መጣያ ሆኖ ቆይቷል፡፡ ነገር ግን አይሁድ ተቀብሮና ተደፍኖ ይቀራል ያሉት የአምላካችን የልዑል እግዚአብሔር ኃይሉና ጥበቡ የሚገለጥበት፣ ድውያን የሚፈወሱበት፣ ሐዘንተኞች የሚጽናኑበት፣ የክርስቲያች መመኪያ የሆነው ቅዱስ  መስቀሉ በተአምራት ከተቀበረበት እንዲወጣ ፈቃዱ ስለሆነ ለዚህ ምክንያት የሚሆኑትን ንጉሥ ቆስጠንጢኖስንና ቅድስት ዕሌኒን ጊዜው ሲደርስ እግዚአብሔር አስነሣ፡፡

የታላቁ ቆስጠንጢኖስ እናት ንግሥት ዕሌኒ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ መስቀል በኢየሩሳሌም ተቀብሮ ለብዙ ዘመናት መኖሩን ትሰማ ስለ ነበር፤ ያንን በክፉዎች አይሁድ ተቀብሮ የሚኖረውን ቅዱስ መስቀል ከተቀበረበት አስቆፍራ ለማውጣት ስለት ተሳለች፡፡  ‹‹ልጇ ቆስጠንጢኖስ ከአሕዛባዊው ንጉሥ ከቁንስጣ የወለደችው ነውና ልጄ ክርስቲያን ቢሆንልኝ ከቁስጥንጥንያ ኢየሩሳሌም ሄጄ የክርስቶስን ቅዱስ መስቀል ከተቀበረበት አስቆፍሬ አወጣዋለሁ›› ብላ ስእለት ተስላ ነበር፡፡

ነገር ግን ታሪኩን ጠይቃ እንደሰማችው መሬት ውስጥ የተቀበረውን ቅዱስ መስቀል ስፍራውን እንዴት አገኘዋለሁ የሚል አሳብ ሁልጊዜ ያስጨንቃት ስለነበር፡፡ እናቱን ስለሚያስጨንቃት ስለ መስቀሉ ነገር ለቆስጠንጢኖስ አንድ ታላቅ ተአምር ተፈጸመለት፡፡  እሱም በሦስት መቶ አሥራ ሁለት (፫፻፲፪) ዓ.ም ቆስጠንጢኖስ ከጠላቱ ከመክስምያኖስ ጋር በሚልቪያን ብሪጅ የጦር ሜዳ ላይ ከመሰለፉ በፊት ሊዋጋ እየተዘጋጀ ሳለ እንዴት አድርጎ ጠላቱን ተዋግቶ ማቸነፍ እንዳለበት ሲያወጣ ሲያወርድ አንድ በከዋክብትና በብርሃን የተሞላ መስቀል ከሰማይ ወደ ንጉሡ ቀረበ፡፡ በዚህ ብርሃን በተሞላ መስቀል ላይም ‹‹በዝንቱ ትእምርተ መስቀል ትመውዕ ፀረከ፤ በዚህ የመስቀል ምልክት ጠላትህን ታቸንፋለህ›› የሚል እጅግ የሚያበራ ጽሑፍ በሰማይ ላይ ተመለከተ፡፡

ቆስጠንጢኖስ ይህንን በራዕይ እንዳየ ወዲያውኑ መስቀሉ እግዚአብሔር በቸርነቱ የሰጠው ኃይል መሆኑን ተገንዝቦ በክርስቶስ በማመን ተጠመቀ፡፡ ምክንያቱም እናቱ ከልጅነቱ ጀምሮ ስለ ክርስትና ሃይማኖት ብዙ ነገር ስታስተምረው ቆይታለችና ለማመንና ክርስቲያን ለመሆን ብዙም አልተቸገረም፡፡ ያን እዚአብሔር ያሳየውን ጠላቶቹን ድል የሚያደርግበትን የመስቀል ምልክት በሰንደቅ ዓላማው ላይ በየጦር ሠራዊቱ ደረትና ልብስ፣ በየፈረሱ አንገትና በየመሣሪያው ሁሉ በጋሻቸው፣ በጦራቸው እንዲያደርጉ አዋጅ አስነገረ፡፡ የወርቅ መስቀል አስቀርጾም ከሠራዊቱ ፊት አስይዞ ዘመተ፡፡

ከዚያ  በኋላ  ክተት  ሠራዊት  ምታ  ነጋሪት  ብሎ  ዘመተባቸው፡፡  በውጊያው  ሰዓት በዲዮቅልጥያኖስና በመክሲምያኖስ ላይ አድረው ደም ያፈሱ የነበሩት አጋንንት በመስቀል ፊት መቆም አልቻሉምና ድል ሆኑ፡፡ ቆስጠንጢኖስም በመስቀሉ ምልክት ምክንያት ኃይለ አግዚአብሔርን ገንዘብ ስላደረገ እየተከተለ አጥፍቷቸዋል (ቆላ ፪፥፲፭)፡፡ ንጉሥ መክስምያኖስም በጦርነቱ በመገደሉ ቆጠንጢኖስ የእርሱን ቦታ ጠቅልሎ በመያዝ የሮማ ግዛት ብቸኛ ቄሳር አውግስጦስ ተባለ፡፡ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ያ ወደ ጦር ሜዳ ለመሄድ ሲዘጋጅ ያየው የመስቀል ምልክትና ያስገኘለት ድል የክርስትናን ሃይማት የበለጠ እንዲወደድና እንዲያስፋፋ ብሎም ንጉሡ አይቀር ባመነበት በክርስትናው እንዲጠነክር፣ ክርስቲያኖችንም አብዝቶ እንዲወድ አድርጎታል፡፡ እንዲያውም ከዚያ በኋላ የቆስጠንጢኖስ የጦር ሠራዊት የሚለየውና መታወቂያ ምልክቱ መስቀል ሆነ፡፡

ይህንን ፈለግ የተከተሉት አባቶቻችንም መስቀልን በሚለብሱት ልብስ  ላይ  በመጥለፍ፣ በቤታቸው ጉልላት ላይ በማድረግ፣ በፈረሳቸው መጣብር ላይ በማስጌጥ፤ በጦራቸው ጫፍ በመሰካት፣ በአንገታቸው ማተብ በማንጠልጠልና በሰውነታቸው ላይ በመነቀስ የሕይወታቸው

መሠረት የደኅንነታቸው ዋልታ መሆኑን መስክረዋል፡፡ እንደነ ቅዱስ ላልይበላ ያሉ አባቶቻችን መስቀሉን በአስደናቂ ሁናቴ የቤተክርስቲያን መሠረትና ጉልላት አድርገው በሁለመናቸው አክብረውት በዘመናቸው ሁሉ ተመላለሱ፡፡ በመስቀሉ ኃይልም ደዌ ጸንቶባቸው የነበሩ ጤናቸውን አግኝተዋል፡፡ እውር የነበሩ አይተዋል፡፡ ልምሾም የነበሩ ተራምደዋል፡፡ በመሆኑም አባቶቻችን የክርስቶስን መስቀል የሚያፈቅሩት ሰይጣን ድል የሆነበት፤ የጠብ ግድግዳ የፈረሰበት ሰላማችን መሆኑን ስለተረዱ ነው፡፡ ምክንያቱም መስቀል ሰይጣን እራስ እራሱን የተቀጠቀጠበትና የተሸነፈበትን ሥልጣኑን የተገፈፈበት የክርሰቶስ ዙፋን ነውና፡፡

መስቀል  ሰይጣን በተንኮሉ በሰው ልጆች ላይ ያመጣው ሞት የሻረበት በመሆኑና ሰይጣን በሰው ልጆች ላይ የነበረውን የገዢነት ሥልጣኑን ያጣበት ስለሆነ አጥብቆ ይፈራዋል፡፡ ስለዚህም አባቶች መስቀሉን ከፊት ከኋላ ደጀን አድርገው ሰይጣን ያደረባቸውን ሠራዊቶች ድል አድርገዋል፡፡ በሀገራችን ኢትዮጵያም በአድዋ ላይ የሆነው ይኸው ነው፡፡ በመስቀሉ ኃይል ተማምነዋልና የመስቀል ምልክት (መስቀል) አናቱ ላይ (ከጫፉ ላይ) ባለው ጦርና ጎራዴ ብቻ እሳት የሚተፋ መትረየስ የታጠቁ የፋሽስት ኢጣሊያን ሠራዊት ማረኩ፡፡

የመስቀሉ ጠላት የሆነው ካቶሊካዊው ወራሪ በዘመናዊ የጦር መሳሪያ የኢትዮጵያን ዳር ድንበር በኃይል ሰባብሮ ወደ ውስጥ በመግባት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ምሽግ ለማድረግ ቢሞክርም አባቶቻችን እግዚአብሔርን ተማምነው የመስቀሉን ምልክት አድርገው የተኮሱት የመድፍ ጥይት ዘመናዊ በሆነው በጠላት መድፍ አፍ ውስጥ ገብቶ የሠራውን ምሽግ ንዶታል፡፡ ስለዚህ ምን ጊዜም ቢሆን ጠላት የሚንቀው መስቀል ለእኛ ኃይላችን፣ መመኪያችን፣ ሰላማችን፣ ማቸነፊያችን ነውና እናከብረዋለን፡፡

ወደቀደመ ነገራችን እንመለስና በመስቀሉ ኃይል በተገኘው ድል መሠረት ቆስጠንጢኖስ ጠንካራ ክርስቲያን ስለሆነ በግዛቱ ሁሉ ጣኦት አምልኮ አከተመለት፡፡ ይመለኩ የነበሩ ጣኦታት እንዲፈርሱ እነዚህ አላውያን ነገሥታት አንጸዋቸው የነበሩት አብያተ ጣኦታት እንዲዘጉና እንዲቃጠሉ ከንጉሡ ቆስጠንጢኖስ ትእዛዝ ወጣ፡፡ ዘመነ ሰማዕታት እየተባለ የሚጠራውምክርስቲያኖች ይገጠማቸው የነበረ የከፋ እንግልትና መከራ እንዲቆም ተደረገ፡፡ በነ ዲዮቅልጥኖስና መክስምኖስ ዘመን ፈርሰው፣ተቃጥለውና ተዘግተው የነበሩ አብያተ ክርስቲያናት ተከፈቱ፣ የክርስቲያኖች የስቃይና የእንግልት ሕይወት በሰላም ተቀየረ፡፡ ምክንያቱም ታላቁ ቆስጠንጢኖስ የሮም ንጉሠ ነገሥት ከሆነ በኋላ ከሦስት መቶ(፫፻) ዓመታት በላይ ክርስቲያኖች አጥተውት የነበረውን ነጻነትና መብት መለሰላቸው፡፡ ለክርስቲያኖች ክብርና ሰላም እንዲሆንላቸውም አዋጅ አወጀ፡፡

ንግሥት ዕሌኒ ስእለቷ ስለሰመረላትና የልጇ የንጉሥ ቆስጠንጢኖስም ነገር ከጠበቀችው በላይ በሃይማኖቱ ጠንካራና ክርስቲያኖችን ወዳድ ስለሆነ እጅግ ተደሰተች፡፡ በተፈጠረላት ምቹ ሁኔታ የገባችውን ስእለቷን ለመፈጸም ተነሣች፡፡

ንግሥት ዕሌኒ ባገኘችው መልካም አጋጣሚ ለመጠቀም በሦስት መቶ ሃያ ስድስት(፫፻፳፮) ዓ.ም ሠራዊት አስከትላ የጌታችንን ቅዱስ መስቀሉን ከተቀበረበት ቦታ ፈልጋ ለማስወጣት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደች፡፡ በቦታውም በደረሰች ጊዜ መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ ያውቁት የነበሩት ክርስቲያኖች በሰብአ (፸) ዓ.ም በጥጦስ ወረራ ከኢየሩሳሌም ተሰድደው ስለነበር መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ በቀላሉ ልታገኘው አልቻለችም ነበር፡፡ ስለሆነም መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ እንዲያሳዩአት ታሪክ የሚያውቁ የአካባቢው የአይሁድ ሽማግሌዎችን እየጠየቀች ነገር ግን በቶሎ የሚነግራት ብታጣም ስታፈላልግ ቆይታ ከብዙ ድካም በኋላ አንድ የአይሁድ ሽማግሌ (አረጋዊ) ኪራኮስ የሚባለውን በተጠቆመችው መሠረት አገኘችውና መስቀሉ የተቀበረበትን ቦታ እንዲነግራት በብዙ ጥበብ ተጠቅማ ጠየቀችው፡፡

እርሱም ‹‹አባቶቻችን ሲናገሩ እንደሰማነው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን በቀበሩበት ቦታ ገቦታ በሚባለው ይኸውም ጎሎጎልታ ነው የከበረ መስቀሉን አባቶቻችን በዚያ ቀበሩት ሲሉ ሰማን፡፡ የከበረ የክርስቶስን መስቀል አይሁድ ከቀበሩት በኋላ የኢየሩሳሌምን ሰዎች ሁሉንም ሕዝብ ትልቁንም ታናሹንም ቤታቸውን የሚጠርጉ ሁሉ የቤታቸውን ጥራጊ ጉድፋቸውን በጌታ ኢየሱስ መቃብር ዕፀ መስቀሉን በቀበሩበት ጎልጎታ በሚባል ቦታ ወስደው በዚያ እንዲጥሉ አዘዟቸው ይሉ ነበር›› አላት፡፡ ዕሌኒ ንሥትም አረጋዊ ኪራኮስን የጌታችንየክርስቶስ መስቀል ከተቀበረ ምን ያህል ዓመት ይሆናል? አለቸው፡፡ ኪራኮስም ቅድስት ዕሌኒን እመቤቴ ሆይ አንቺ ወደዚህ እስከ ደረስሽበት ጊዜ ሦስት መቶ(፫፻) ዓመት ሆነው፡፡ ሰዎችም ሁሉ በላዩ የሚጥሉት የየቤት ጥረጊያቸውና ጉድፋቸው ታላቅ ኮረብታ እስኪሆን ድረስ የኢየሩሳሌም ሰዎችም ሁሉ የሚጥሉት ጉድፍ በሰው ክንድ አምስት መቶ ያህል ከፍ ከፍ አለ እመቤቴ ሆይ የጌታ ክርስቶስ የመስቀሉ ነገር እንዲህ ነው አላት፡፡

ንግሥት ዕሌኒም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል የተቀበረበትን ሥፍራ ስለሰማች እጅግ ደስ አላት፡፡ ስትናፍቀው የነበረውን መስቀሉ የተቀበረበትን አካባቢ (ሥፍራ) የሚያመላክት

ፍንጭ ስላገኘች እግዚአብሔርን እያመሰገነች እንዲህ ስትል ጸለየት ‹‹እኔ ከሩቅ ሀገር የከበረ መስቀልህን ለመፈለግ መጥቻለሁና ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ለሚጠሉኝ ጠላቶቼ አጋንንትና አንተን ለሰቀሉ ፈጽሞ የከበረ መስቀልህንም ለቀበሩ ዐመፀኞች አይሁድ መሳቂያና መዘባበቻ አታድርገኝ›› ብላ ጸለየች፡፡ እንዲህም ወደ ልዑል አምላክ ስትጸልይና ስትለምን ወዲያውኑ ‹‹በከበረ ደሜ የተቀደሰ መስቀሌ በመንግሥትሽ ወራት ዕሌኒ ሆይ ይገኝልሻል፣ ይገኝልሻል፣ ይገኝልሻል የሚል ቃል ሦስት ጊዜ ከሰማይ ሰማች አገልጋዬ ዕሌኒ ሆይ ከጥቂት ወራቶች በኋላ የፈለግሽውን ታገኚአለሽና ፈጽሞ ደስ ይበልሽ›› አላት፡፡

ከዚያም በኋላ መስቀሉ የተቀበረበትን ትክክለኛ ቦታ ለይቶ ለማወቅ የቆሻሻው ጥርቅም እንደ ተራራ ገዝፎ ስለነበር አስቸጋሪ ስለሆነባት እንዴት አድርጋ የክርሰቶስ መስቀል የተቀበረበትን ሌሎች ከጎኑ ካሉት ተራሮች መለየት እንደምትችል ከአረጋዊው ኪራኮስ በተነገራትና እገዚአብሔርን በጸሎት ጠይቃ ባገኘችው መልስ መሠረት ካህናቱና ሕዝቡን ሰብስባ በእንጨት ደመራ አስደምራ ጸሎትና ምህላ ካስደረሰች በኋላ ዕጣኑን ጨምራ ደመራውን በእሳት ለኮሰችው፡፡

በመሆኑም በእሳት ከተለኮሰው ደመራ የሚወጣው ጢስ ወደ ላይ ወጥቶ ወደታች ወደ ጎልጎታ በመመለስ መስቀሉ የተቀበረበት ቦታ ላይ በመተከል ያለበትን ቦታ በጣት ጠቅሶ እንደማሳየት ያህል አመለከተ፡፡ ንግሥት ዕሌኒም እሊህን ምልክቶችና እውነት የሆኑ ሥራዎችን ባየችና በተመለከተች ጊዜ ድምጿን ከፍ አድርጋ እንዲህ እያለች ዘመረች፡፡‹‹እውነት በእውነት ያለሐሰት የጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በላዩ የከበረ ደሙ የፈሰሰበት መስቀሉ የተቀበረበት ቦታው ይህ ነው›› እያለች በደስታ እግዚአብሔርን አመሰገነች፡፡

ከዚህ በኋላ ንግሥት ዕሌኒ ለአገልጋዮቿና ለሠራዊቶቿ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ዕፀ መስቀሉ ለተቀበረበት ቦታ ምልክቱ ይህ ነው አለቻቸው፡፡ በመሆኑም ንግሥት ዕሌኒ የጢሱን ስግደት ተመልክታ ጢሱ ያረፈበት ቦታ ቅዱስ መስቀሉ የተቀበረበት እንደሆነ በማመን ቅዱስ መስቀሉ ከዚህ ቦታ አለ ብሎ ሲጠቁመን ነው በማለት ሳትጠራጠር በመስከረም ወር በዐሥራ ሰባተኛው ቀን የጌታችን ክርስቶስ ዕፀ መስቀል በውስጡ የተቀበረበት እስከሚገኝ እጅግ ጥልቅ አድርገው ምድሩን ይቆፍሩ ዘንድ ሠራዊቶቿና ሕዝቡን ሁሉ አዘዘቻቸው፡፡

ከዚህ በኋላ ጭፍሮቿና ሁሉም የአይሁድ ሕዝብ መስቀሉን ለማግኘት መስከረም ዐሥራ ሰባት ቀን መቆፈር ጀመሩ፡፡ አስቀድመውም በላዩ የተጣለና የተደፋ እንደ ኮረብታ ሆኖ መጠኑ በሰው ክንድ አምስት መቶ የሆነው የአይሁድን ጉድፋቸውንና ጥራጊያቸውን አነሡ፡፡ ከዚያም ቀጥለው በሰው ክንድ ዘጠና ዘጠኝ ያህል ወደታች አጥልቀው በቆፈሩ ጊዜ ጠንካሮች የሆኑ የተጣመሙ ደንጊያዎችን አስቀድሞ አገኙ፡፡ እንዚያንም ደንጊያዎች ባነሱ ጊዜ ከጥልቁ ጉድጓድ ውስጥ ታላቅ ብርሃን  ወጣ  እንደ  ፀሐይም  አንፀባረቀ፡፡  በዚያንም  ጊዜሁለት  መስቀሎችን  አግኝተው አወጧቸው፡፡ ቀጥሎም የጠነከሩና የጠመሙ ደንጊያዎችን አወጡ፡፡ ከዚህም በኋላ ከአምስት ችንካሮች ጋር ሌላ መስቀልን አገኙ እሱም ጌታችን የተሰቀለበት ቅዱስ መስቀሉ ነው፡፡

እሊህም ችንካሮች፡- ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ ሮዳስ የሚባሉ ናቸው፡፡ ሰፍነጉን ራሱን የመቱበት ሽመሉን፣ ከለሜዳውን የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስን የገረፉበትንና ያሰቃዩበትን ዕቃዎች ሁሉን ከቅዱስ መስቀሉ ጋር አገኙ፡፡ ይህም የሆነው ቁፋሮው መስከረም ፲፯ ተጀምሮበመጋቢት ወር በ፲ኛው ቀን ነው፡፡ ይህም ማለት በሦስት መቶ ሃያ ሰባት (፫፻፳፯) ዓ.ም በመጋቢት ፲ ቀን ቅዱስ መስቀሉ ከተቀበረበት ቦታ ወጣ ማለት ነው፡፡

ይሁን እንጂ ወዲያውኑ ቆፍረው እንዳወጡት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ጋር ሁለቱ ወንበዴዎች የተሰቀሉባቸውንም መስቀሎች አብረው ስላገኙ ቅዱስ መስቀሉን መለየት አልቻሉም፡፡ በእርግጥ ታሪኩ እንደሚነግረን ከተገኙት ሦስት መስቀሎች መካከል አንደኛው መስቀል ልክ ከጉድጓዱ ሲያወጡት ቦግ ብሎ ብርሃን ፈነጠቀበትና አካባቢውን ሁሉ ብርሃን አጥለቀለቀው በማለት ያስረዱናል፡፡

ይሁን እንጂ በቅዱስ መስቀሉ ላይ የብርሃን ምልክት ቢታይም በእውነት ክርስቶስ የተሰቀለበትን መስቀል  ሁለቱ  ወንበዴዎች  ከተሰቀሉባቸው መስቀሎች ለመለየትና ለማረጋገጥይቻል  ዘንድ የኢየሩሳሌም ጳጳስ የሆኑት አቡነ መቃርዮስ ሦስቱንም መስቀሎች በተራ እንዲያስቀምጡአቸውና አንድ የሞተ ሰው አስክሬን እንዲያመጡ አዘዙ፡፡ የሞተውን ሰው አስከሬንም በአንደኛው መስቀልና በሁለተኛው መስቀል ላይ አደረጉት የሞተው ሰው አልተነሣም፡፡ በሦስተኛው መስቀል ላይ ቢያስቀምጡት ግን ያ የሞተ ሰው አፈፍ ብሎ ተነሣና ለክርስቶስ መስቀል ምስጋና አቀረበ፡፡ በቅዱስ መስቀሉ ሌሎችም ድንቆች ተአምራቶች ተፈጸሙ፡፡ ዕውሮችን አብርቷል፣ ድውያን

ፈውሷል፣ ጎባጦችን አቅንቷል፣ በነዚህና መሰል ገቢረ ተአምራቶች ክርስቶስ የተሰቀለበትና የከበረ ደሙ የፈሰሰበት ቅዱስ መስቀሉ ከሌሎች ተለይቶ ታውቋል፡፡

በዚያም የነበሩ ሰዎች ሁሉ እጆቹንና እግሮቹን ለሕማም በዕፀ መስቀል ላይ የዘረጋ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ ሕዝቡ ሁሉ በተገለጡት ተአምራቶችና በክርስቶስ መስቀል በተፈጸሙት ተአምራቶች ደስታቸው እጅግ ጥልቅ ስለነበር በእንባ ጭምር የደስታ ስሜታቸውን አንፀባርቀዋል፡፡ ቅድስት ዕሌኒም በዚህ ጊዜ አሳቧና ምኞቷ ስለተፈጸመላትና በቅዱስ መስቀሉ የተደረጉትን ተአምራቶች በዐይኖቿ ማየት በመቻሏ ደስታዋ ወደር አልነበረውም፡፡ እግዚአብሔርንም በብዙው አመሰገነች፡፡ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልም ሰገደች፡፡ ጭፍሮቿም ሆኑ የተሰበሰቡ የኢየሩሳሌም ሕዝቦች ሁሉ ለቅዱስ መስቀሉ በታላቅ አክብሮት ሰገዱ፡፡ መስቀሉንም እየዳሰሱ ተሳለሙት፣ ሕሙማንም እየዳሰሱትተፈወሱ፣ የኢየሩሳሌሙ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ መቃርዮስም እጅግ ደስ ብሏቸው ፈጣሪያችንን አመሰገኑ፡፡

ቀኑ መሽቶ ጨለማ በሆነ ጊዜም ብፁዕ አቡነ መቃርዮስና ንግሥት ዕሌኒ ሠራዊቱና ሕዝቡ ሁሉ በሰልፍ የችቦ መብራት ይዘው እየዘመሩ ቅዱስ መስቀሉን ወስደው በአንድ የጸሎት ቤት አስቀመጡት፡፡ ከዚህ በኋላ ንግሥት ዕሌኒ እንዲህ ስትል ካህናቱን አዘዘቻቸው ‹‹የከበረ ዕፀ መስቀልን ከወርቅ በተሠራ ግምጃ አጎናጽፉት ብሩህ በሆነ ልብስም ጠቅልሉት በሰማያዊ ዕንቊ ሸፍናችሁም ከወርቅ ዐልጋ ላይ አውጡት ከወርቅ ሣጥንም ውስጥ አስገቡት አለቻቸው›› እነርሱም እንደታዘዙት አድርገው ቅዱስ መስቀሉን በክብር አኖሩት፡፡ ቅድስት ዕሌኒ በመስቀሉ መገኘት ደስ እየተሰኘችና እግዚአብሔርን እያመሰገነች በቅዱስ መስቀሉ ስም በኢየሩሳሌምና በሮሜ አገር ቤተክርስቲያንን አንፃለች፡፡ በኢየሩሳሌምም አስቀድማ በከበረ መስቀል ስም ታላቅ ቤተ ክርስቲያን አንጻለች፡፡ ቀጥላም በእመቤታችን ስም ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አነጸች፡፡ ንግሥት ዕሌኒ ያሠራቻቸውን አብያተ ክርስቲያናት በወርቅ፣ በብር፣ በዕንቊ መርገድ፣ ጳዝዮን በሚባሉ ዕንቊዎች፣ አስጌጠቻቸው፡፡

ቅድስት ዕሌኒ ለከበረው ለክርስቶስ መስቀል እጅግ የሚያምር ቤተ ክርስቲያን ካሳነጸች በኋላ በቅዱስ መስቀሉ ስም ታላቅ በዓልን በማድረግ ለድሆችና ለምስኪኖች፣ ለባልቴቶችና ለሙት ልጆች ታላቅ ምሳን አዘጋጀች፡፡ ስለጌታችን ክርስቶስ መስቀልም ስለ ክብሩ መኳንንቶችን መሳፍንቶችንና የሀገር ሰዎችን ሁሉ ጠራቻቸው፡፡ ብዙ ላሞችንና ሰንጋዎችን፣ በጎችንና ፍየሎችን አሳረደች፡፡ በዚያች ዕለትም የታረዱት የቁጥራቸው መጠን ላሞች ዘጠኝ ሺህ፣ በጎች

ሰባ ሺህ፣ ፍየሎች ሰባ ሺህ፣ ዶሮዎች ዘጠኝ ሺህ ናቸው፡፡ በዚህ መልኩ በዓልን አድርጋ በቅዱስ መስቀሉ ስም ብዙዎችን መገበች፡፡

ንግሥት ዕሌኒ እንዲህ ባው መልካም ሥራ ከኖረች በኋላ በሦስት መቶ ሃያ ስምንት (፫፻፳፰) ዓ.ም በክብር አርፋለች፡፡ ታላቁ ቆስጠንጢኖስም በሦስት መቶ ሠላሳ ሰባት(፫፻፴፯) ዓ.ም ግንቦት ሃያ ሁለት (፳፪) ቀን የጰራቅሊጦስ ዕለት በኀምሳ አራት (፶፬) ዓመቱ በነገሠ በሠላሳ አንድ (፴፩) ዓመቱ በክብር ዐረፈ፡፡ በመሆኑም እናትና ልጅ በሠሩት ክርስቲያናዊና ሐዋርያዊ ተግባር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስታስታውሳቸው ትኖራለች፡፡ ቅዱስ መስቀሉ የተገኘበትንም መጋቢት ፲ ቀን ስብሐተ እግዚአብሔር በማድረስ የመስቀሉን ኃይል እየመሰከረች አክብራ ትውላለች፡፡

ከቅዱስ መስቀሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን አሜን፡፡

“ቅድስት”

በቀሲስ ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት ቅድስት ይባላል፡፡  እንደሚታወቀው የዐቢይ ጾም ሳምንታት ሁሉ ስያሜ አላቸው፡፡ ስያሜአቸውም   የእግዚአብሔር ባሕርይ የሚገለጽባቸውና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን ስለ ማዳኑ ስለተቀበለው ጸዋትወ መከራ የሚያስረዱ ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ሳምንት ዘወረደ፣ሙሴኒ፣ሕርቃል የሚሉ መጠሪያዎች ያሉት ሲሆን ዘወረደ ማለት መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆነ፣ከሰማየ ሰማያት ወረደ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ ሕግ መጽሐፋዊንና ሕግ ጠባይዓዊን እየፈጸመ ከኃጢአት በቀር ሁሉን እያደረገ በተለይም ለእኛ አብነት የሚሆንባቸውን ሁሉ እየሠራ ቀስ በቀስ አደገ ማለት ነው፡፡

በቃሉ ትምህርት ደዌ ነፍስን በእጁ ተአምር ደዌ ሥጋን ከሰው ልጅ እያራቀ ፍጹም አምላክ ሲሆን የሰውነትን ሥራ ሠራ፡፡ፍጹም ሰው ሲሆን የአምላክነትን ሥራ ሠራ፡፡ በመሆኑም “ዘወረደ” አምላክ ሰው በመሆን የፈጸመልንን የማዳኑን ሥራ የምንመሰክርበት ነው፡፡

ሌላው “ሙሴኒ” ብለን ሳምንቱን መጥራታችን ሊቀ ነቢያት ሙሴ እንደሚታወቀው እስራኤልን ከግብጽ ባርነት ነፃ አውጥቶ ባሕር ከፍሎ ያሻገራቸው የእግዚአብሔር ሰው ነው፡፡ ሙሴን ለዚህ አገልግሎት የመረጠው ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ የሙሴም መሪነት የተፈጸመው በእግዚአብሔር ኃይል በቃሉ ነው፡፡ ሙሴ እስራኤል ከግብጽ እንዳወጣ ሁሉ መድኃኒታችን ኢሱስ ክርስቶስም አዳምንና የልጅ ልጆቹን ሁሉ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሲኦል ወደ ገነት የመለሰ ነውና ሙሴኒ ተብሎ ተሠየመ፡፡

በሌላ መልኩ “ሕርቃል” መባሉም  ሕርቃል የሮም ንጉሥ በነበረበት ሰዓት ክርስቲያኖች ቅዱስ መስቀሉን በፋርሳውያን ተነጥቀው ስለ ነበር ክርስቲያኖችን ረድቶ መስቀሉን ከፋርሳውያን እጅ በጦርነት አሸንፎ ለክርስቲያኖች ለማስመለስ በሚያደርገው ውጊያ ላይ ክርስቲኖች የጾሙለት የመስቀሉንም መመለስ በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን የጠየቁበት ስለሆነ ጾመ ሕርቃል ተብሎ ተሰይሟል፡፡

የዐቢይ ጾም የመጀመሪያው ሳምንት (ዘወረደ) ቀጥሎ ያለው ሁለተኛው ሳምንት ቅድስት ይባላል፡፡ ቅድስት መባሉም አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር በባሕርዩ ቅዱስ መሆኑንና  እኛን ለቅድስና የጠራን መሆኑን “እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ” በማለት ለክብር ያጨን መሆናችንን እያሰብን የምናመሰግንበት ሳምንት ነው፡፡ እግዚአብሔር ቅዱስ ነው ስንል የእርሱ ቅድስና ከቅዱሳን መላእክት እና ከቅዱሳን ጻድቃን፣ከቅዱሳን ሰማዕታት ይለያል፡፡ የቅዱሳኑ ሁሉ ቅድስና የጸጋ ነውና፡፡

በባሕርዩ ፍጹም ቅዱስ የሆነ ከማንም ያላገኘው ማንም ያልሰጠውና የማይወስድበት ቅዱስ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ለዚህም ነው ነቢዩ ኢሳይያስ ሱራፌል በቅዳሴያቸው ያለማቋረጥ  ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ብለው የሚያመሰግኑት መሆኑን የገለጸው፡፡ “አንዱም ለአንዱ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች እያለ ይጮኽ ነበር”(ኢሳ.፮፥፫)ይላል፡፡

እግዚአብሔር ቅዱስ በመሆኑ ሰውም በንጽሕና በቅድስና እንዲመስለውና እንዲያገለግለው ይፈልጋል፡፡ ሰንበት እግዚአብሔር ለምስጋና ያዘጋጃት ከሥጋ ሥራ አርፈን የነፍስ ሥራ እንሠራባት ዘንድ የተሰጠችን የተቀደሰች ቀን ናት፡፡ ይህንንም እንድናስብ  የዐቢይ ጾም ሁለተኛው ሳምንት   ቅድስት ተብሎአል፡፡

እግዚአብሔር ከሥራው ሁሉ ያረፈባትን ቀዳሚት ሰንበት ከዕለታት ሁሉ የለያትና የቀደሳት ሲሆን በዚህች ዕለት ከሥጋ ሥራ ሁሉ እንድናርፍባት ቀድሶ ሰጥቶናል ይህቺም ዕለት ከሥነ ፍጥረት ጀምሮ ትታሰብ የነበረች ቢሆንም በኦሪት ሕግ ግን በጉልህ እግዚአብሔር ለሙሴ በሲና ተራራ እስራኤል ይመሩበት ዘንድ  ከሰጠው ሕጎች መካከል አንዱዋ ሆና ተጠቅሳለች(ዘፀ.፳፥፩)፡፡

ሰንበተ ክርስቲያን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ዓለሙን ሁሉ ከሞት ከኩነኔ ለማዳን ሞትን በሞቱ ደምስሶ ወደ ቀደመ ክብራችን በመመለስ ቅድስት ትንሣኤውን ያየንባት ዕለት ሰንበተ ክርስቲያን (እሑድን) የተቀደሰ ሥራ በመሥራት የሰንበትን ቅድስና እያሰብን የምናከብር በመሆናችን ይህ ስያሜ ተሰጥቷል፡፡

                               ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ከፊት ይልቅ ትጉ”(፪ኛ ጴጥ.፩፥፲)

በቀሲስ ኃለ ሚካኤ ብርሃኑ

ክፍል ሁለት

በክፍል አንድ ጽሑፋችን ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “ከፊት ይልቅ ትጉ” በማለት ያስተማረውን መነሻ አድርገን እንዴት መትጋት እንዳለብን እና በምን መትጋት እንደሚገባን የተወሰኑትን ተመልክተን ነበር፡፡ አሁንም ከዚያው ቀጥለን ልንተጋባቸው የሚገቡንን ሐዋርያው ዘርዝሮ ያስተማረንን እንመለከታለን፡፡

በበጎነትም  ዕውቀትን ጨምሩ”

ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለተኛ መልእክቱን ሲጽፍ ራሱን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ባርያ እና ሐዋርያ በማለት ከገለጸ በኋላ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስላገኘነው ጽድቅና ድኅነት  በማብራራት ከዚህ ዓለም የጥፋት ምኞት በመሸሽ የክብሩ ወራሾች እንሆን ዘንድ ስለ ተሰጠን ተስፋ ዕለት ዕለት መትጋት እንደሚያስፈልገን በሰፊው ገልጾታል፡፡ ለዚህም ነው “እናንተ ግን በሥራው ሁሉ እየተጋችሁ በእምነት በጎነትን በበጎነትም ዕውቀትን ጨምሩ” በማለት ልንተጋባቸው የሚገባንን ሁሉ ዘርዝሮ የሚነግረን::

ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳለው በጎነት ዕውቀት ሊጨመርበት ያስፈልጋል፡፡ ዕውቀትም እውነቱን ከሐሰት፣ ብርሃንን ከጨለማ፣ ሕይወትን ከሞት ጣፋጩን ከመራራ የመለየት አቅም እንዲኖረን ያደርጋል፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል “እነሆ እኔ እንደ በጎች በተኲላዎች መካከል እልካችኋለሁ እንግዲህ እንደ እባብ ብልሆች እንደ ርግብም የዋሆች ሁኑ”(ማቴ.፲፥፲፮)በማለት ለቅዱሳን ሐዋርያት ያስተማራቸው፡፡ ብልህነትን ከእባብ የዋህነትን ከርግብ መማር እንደሚገባን በቅዱሳን ሐዋርያት አንጻር ተሰበከልን፡፡ ምክንያቱም በጎነታችን ለሞኝነትና ለመታለል እንዳይዳርገን ሁሉን በመመርመር መፈተን እንድንችል እንጂ በጎነትን ያለ ጥበብና ዕውቀት እናድርግ ብንል ተላላዎች ሊያደርገን ስለሚችል  በበጎነት ላይ ዕውቀት ሊጨመርበት  ያስፈልጋል፡፡

ሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስም የሚሰበክልንን ትምህርት መለየት እና ስለ ማንነታችን በሃይማኖታዊ ዕውቀት መመዘን እንደሚያሻን አስተምሮናል፡፡ “በሃይማኖት ጸንታችሁ እንደሆነ ራሳችሁን መርምሩ፤እናንተ ራሳችሁን ፈትኑ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናንተ ጋር እንዳለ አታውቁምን? እንዲህ ካልሆነ ግን እናንተ የተናቃችሁ ናችሁ” (፪ኛቆሮ.፲፫፥፭) በማለት ራሳችንን በምን ሁኔታ ላይ እንዳለን በእግዚአብሔር ቃል ሚዛን  መፈተሽ የሚያስችል ዕውቀት ሊኖረን እንደሚገባ የሚያስገነዝብ ነው፡፡

“በዕውቀት ንጽሕናን ጨምሩ”

ዕውቀት ብቻ በራሱ አያጸድቅም፡፡ ወደ ጽድቅ ለመምራት ግን በመሳሪያነት ያገለግላል፡፡ ብዙዎች ዐዋቂዎች ነን ባዮች እግዚአብሔርን ማየት አልቻሉም፡፡ በዕውቀታቸው ሳይታበዩ ንጽሕናን ገንዘብ ያደረጉ ቅዱሳን አበው ግን በእግዚአብሔር ጸጋ ከብረው ይኖራሉ፤ ስለዚህ ዕውቀት ንጽሕና ቅድስና ሊጨመርበት ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡

ለዚህም ነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል “ልባቸው ንጹሕ የሆነ ብፁዓን ናቸው እነርሱ እግዚአብሔርን ያዩታልና” (ማቴ.፭፥፰) በማለት የልብ ንጽሕና እግዚአብሔርን ለማግኘት የሚያስችልና ለመንፈስ ቅዱስ ማደሪያነት እንደሚውል  ያስተማረው፡፡ እግዚአብሔር የሰውን ፊት አይቶ ሳይሆን ልባችንን መርምሮ ለእርሱ የሚመች ማንነት እንዲኖረን ይፈልጋል፡፡ ይህንን እውነታ በሃይማኖታዊ ዕውቀት መርምሮ የተረዳ ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ ንጹሕ ልብን ፍጠርልኝ የቀናውንም መንፈስ በውስጤ አድስ” በማለት አስተማረን(መዝ.፶፥፲)፡፡ ስለዚህ ባወቅን ልክ ወደ ንጽሕና ለመድረስ ማቅናት ይኖርብናል፡፡

“በንጽሕና ትዕግሥትን ጨምሩ”

ከላይ እንዳየነው ንጽሕና ያለ ድካም የሚገኝ አይደለም፡፡ በብዙ ድካምና በብዙ ውጣ ውረድ ፈተናን ሁሉ ተቋቁሞ የዐይን አምሮትን እና የልብ ክፉ መሻትን ተቆጣጥሮ ራስን ከኃጢአት በመለየት የሚገኝ ክብር ነው፡፡ ንጽሕና ስንል የልብ ነው፡፡ እሱም በትዕግሥት ጸንተን የምንቆምበት እንጂ ትናንትን ሆነን ዛሬ የማንገኝበት ወይም ዛሬን ሆነን ነገ ላይ የማንውልበት መሆን የለበትም፡፡ ምክንያቱም በነበር የምንተርከው ሳይሆን ሆነን የምንገኝበት ነውና ትዕግሥትን መላበስ ይኖርብናል፡፡

ትዕግሥት ፈተናን በጽናት ለማለፍና በትጋት ለመሻገር ያስችላል፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ “አሁንም ያ ቆሜአለሁ ብሎ በራሱ የሚታመን ሰው እርሱ እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ”(፩ኛቆሮ.፲፥፲፪) በማለት እንዳስተማረን ንጽሕናን በንስሓ ይዘን በትዕግሥት ፈተናዎችን ሁሉ ማለፍ ያስፈልጋል፡፡ አንዳንዴ ፈተና ጠንካራውን ደካማ፣ አማኙን ተጠራጣሪ፣ አሸናፊውን ተሸናፊ ለማድረግ በሰይጣን ታስቦ የሚመጣ ቢሆንም ከፈተና በኋላ የሚገኝ የድል አክሊል እንዳለ በማሰብ ትዕግሥትን ገንዘብ ማድረግ የሠይጣንን አሳብ መቃወም ተገቢ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዘመኑ መጨረሻ እንደደረሰ የሚያሳዩ የመከራ ምልክቶችን ከዘረዘረ በኋላ  “እስከ መጨረሻው የሚታገሥ ግን እርሱ ይድናል” (ማቴ.፳፬፥፲፫) በማለት ትዕግሥትን እስከ መጨረሻው አጽንቶ መያዝ እንደሚገባ አስተምሮናል፡፡

“በትዕግሥት እግዚአብሔርን ማምለክ ጨምሩ”

በወንጌል ትዕግሥትን ያዘወተረ እርሱ ይድናል እንደተባለ ሁሉ እግዚአብሔርን በትዕግሥት ሆነን ስለ ሁሉ ነገር ማመስገን አለብን፡፡ ፈተናዎች ቢበዙብንም እንኳ መታገሥና ለበጎ እንደሚሆን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ጌታችንም በወንጌል “በእኔም ሰላምን እንድታገኙ ይህን ነገርኋችሁ በዓለም ግን መከራን ትቀበላላችሁ ነገር ግን ጽኑ እኔ ዓለሙን ድል ነሥቼዋለሁና”(ዮሐ.፲፮፥፴፫) ብሎ እንዳስተማረን በትዕግሥት ሆነን እግዚአብሔርን ማምለክ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ፍጥረታት መካከል ሰውና መላእክት ለምስጋና እንደተፈጠሩ ሁልጊዜ ማሰብ ይኖርብናል፡፡

እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥረው ስሙን ቀድሶ መንግሥቱን ይወርስ ዘንድ ነው እንጂ እንዲሁ እንደ እንስሳ አየበላና እየጠጣ በዘፈቀደ እንዲኖር አይደልም ስለዚህ የሰው ተቀዳሚ ሥራው ሊሆን የሚገባ እግዚአብሔርን ማምለክ ነው፡፡ ሰው እግዚአብሔርን በማምለኩ የእግዚአብሔር ስጦታ ይበዛለታል፡፡ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ያአጋጃትን የማታልፈውን መንግሥቱን የሚያወርሰው ስሙን ቀድሶ ሕጉን ጠብቆ ለኖረ ሁሉ እንደሆነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡

“እግዚአብሔርንም በማምለክ ወንድማማችነትን ጨምሩ”

ማንም ሰው እግዚአብሔርን አመልካለሁ ቢል የወንድማማችነት ፍቅር ሊኖረው ይገባል፡፡ አንተ ትብስ እኔ ተባብለው መረዳዳትና መተሳሰብ ተገቢ ነው፡፡ እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ ወንድምን መርገም አይገባም፡፡ ጠላቶቻችሁን ውደዱ ለሚያሳድዷችሁ ጸልዩላቸው… የተባለውን የወንጌሉን ቃል መፈጸም ያሻል፡፡

የእግዚአብሐየር ልጆች የሚታወቁበት እውነተኛ ፍቅር ምን መምሰል እንዳለበት ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ “የእግዚአብሔር ልጆችና የዲያብሎስ ልጆች በዚህ የተገለጡ ናቸው ጽድቅን የማያደርግና ወንድሙን የማይወድ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደልም” (፩ኛዮሐ.፫፥፲) በማለት ጽድቅን ማድረግ ወንድምን መውደድ እንደሆነ አስረድቶናል፡፡

ሃይማኖታችንን ጠብቀን ምግባራችን አቅንተን ለመኖር የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡

ይቆየን…

ወጣትነትና ታማኝ አገልጋይነት

የሰው ልጅ በዚህች ምድር በሚኖረው ቆይታ ብዙ ትጋት፣ ብዙ ኃይልና ብዙ መነሳሳት የተሞላበት ዘመን የወጣትነት ዘመን ነው፡፡ የሰው ልጅ ከሌላው ጊዜ በተለየ አዲስ ግኝቶችን ለማግኘት፣ እጅግ ከባድና ውስብስብ የሚመስሉ ጉዳዮችን በድፍረት ለመጀመርና ለመሞከር ታላቅ ወኔና ድፍረት የታጠቀበት ዘመን የወጣትነት ዘመን ነው፡፡ የማወቅ፣ የመመራመር ጉጉት፣ የማገልገል ልዩ ትጋትና ቁርጠኝነትን የተላበሰ ዘመንም የሚታየው በወጣትነት ነው፡፡ አካላዊ፣ ማኅበራዊ፣ መንፈሳዊ፣ ብሎም ምጣኔ ሀብታዊ ለውጦች በስፋት የሚስተናገዱበት፣ በውስብስብ ፈተናዎች የተሞላበት ዘመን ቢኖር የወጣትነት ዘመን ነው፡፡ ችኩልነት፣ እብሪተኝነት፣ አልታዘዝ ባይነት የሚፈታተኑት በወጣትነት ነው፡፡ ሉላዊነት አስተሳሰብ፣ ለረቀቀ የቴክኖሎጂ አቅርቦት፣ ለባህል ብረዛ፣ ሥራ አጥነት፣ ለቤተሰብ ጫና የሚጋለጠውም በወጣትነት ዘመን ላይ ነው፡፡

ይህንን ወጣትነት ብዙዎች እንደተጠቀሙበት ሁሉ ብዙዎችም መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ተብለው “እንግዲህስ ምድራችንን እንዳታቦዝን ቁረጣት” (ሉቃ.፲፫፥፮) እንደተባለች እንደዚያች በለስ የመቆረጥ ፍርድ ተፈርዶባቸዋል፡፡ በዚህ የወጣትነት ዘመን አቤል የፈጣሪውን ንጹሐ ባሕርይነት ተረድቶ ቀንዱ ያልከረከረውን፣ ጥፍሩ ያልዘረዘረውን፣ ጸጉሩ ያላረረውን ንጹሕ የመሥዋዕት ጠቦት በንጽሕና አቅርቦ በእግዚአብሔር ዘንድ ሞገስን እንዳተረፈበት ሁሉ፤ ወንድሙ ቃየልም በንዝሕላልነትና ግድየለሽነት ከሕይወት መስመር ወጥቶ ተቅበዝባዥነትን ተከናንቧል።(ዘፍ.፬፥፫፲፭)፡፡ በወጣትነት ዮሴፍ እንደ ወርቅ በእሳት ተፈትኖ ንጽሕናውን አሳይቶበታል፤ በዚሁ ወጣትነት ራሱን ለታይታና ለይስሙላ ባለሆነ ፍጹም ትሕትና ከወንድሞቹ ሁሉ በታች ዝቅ አድርጎ በንግሥና ከፍ ከፍ ብሎበታል፡፡(ዘፍ.፴፱፥፩)፡፡ በዚያም በምድርና በሰማይ ሠላሳ፣ ስድሣ፣ መቶም ያማረ ፍሬ አፍርቶ ዝገት የማይበላውን፣ ሌቦች የማይሰርቁትን መዝገብ አከማችቶበታል፡፡

በዚሁ የወጣትነት ዘመን እንደ ጢሞቴዎስ ያሉት ትጉሃን ደቀ መዛሙርት በትጋት የመምህራቸውን ፈለግ ተከትለው ለክርስቲያን ወገኖቻቸው ተርፈውበታል፣ በመምህራቸውም እንዲህ ተወድሰዋል “በአንተ ያለውን ግብዝነት የሌለበትን እምነትህን አስባለሁ” (፪ኛጢሞ. ፩፥፲፭):: ወጣትነት ከሰማያዊው ክብር ይልቅ ምድራዊውን ድሎት የመረጡ እነ ዴማስም እንዲህ ተብለዋል “ዴማስ ይህንን የዛሬውን ዓለም ወድዶ እኔን ተወኝ፤ ወደ ተሰሎንቄም ሄደ”  (፪ኛጢሞ. ፬፥፲)፡፡ በዚሁ የወጣትነት ዘመን ነው እንደ ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ያሉት መከራና ግፍን ሳይፈሩ በጥብአትና በእምነት ለታላቅ ድልና መንፈሳዊ አክሊል የበቁት፡፡ እንዲያው በጥቅሉ ይህንን የወጣትነት ዘመን ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ አስገዝተው ለክብር ሞት፣ ለዘለዓለም ሕይወት የበቁ ብዙዎች እንደሆኑ ቅዱሳት መጻሕፍት ይዘክራሉ፣ አበው ሊቃውንትም ያስተምራሉ፡፡

በውኑ የኛስ የወጣትነት ዘመን የትጋት ነው? ከላይ እንደተጠቀሱት ደጋግ አበው ቅዱሳን የተሰጠንን መክሊት ሠርተን፣ ደክመን፣ ወጥተን ወርደን ለማትረፍ እየጣርንበት ነው? ወይስ የተሰጠንን ጸጋና መክሊት ቀብረን ያው ያለን እንኳ ተወስዶብን ለቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ወደማይጠፋ እሳት ለመጣል እየጠበቅን ነው? በእውኑ በወጣትነቱ ደግና ታማኝ አገልጋይ (ገብር ሔር) ማን ነው? ወጣቶች ወደ መንፋሳዊ አገልግሎት እንዳይቀርቡስ እንቅፋት የሆናቸው ምንድን ነው? ተግተው ለአገልግሎት የመጡት ወጣቶችስ እየገጠማቸው ያለው ፈተናና ተግዳሮት ምንድን ነው? ወጣትና ታማኝ መንፈሳዊ አገልጋይ ለመሆንስ ምን ማድረግ አለባቸው?

የመንፈሳዊ አገልግሎት እንቅፋቶች በዘመናችን አብዛኛዎቹ ወጣቶች ከእግዚአብሔር ቤት እየሸሹ ውሎና አዳራቸው ለመንፈሳዊ ሕይወታቸው ብቻ ሳይሆን ለሥጋዊ (ዓለማዊ) ሕይወታቸው እንኳ ወደማይጠቀሙበት አቅጣጫ በማምራት ከዓላማቸው ተሰናክለው ለጤና መታወክ በሚያበቋቸው አልባሌ ቦታዎች ሆኗል፡፡ ድምጿን ከፍ አድርጋ ለምታጠራ ቤተ ክርስቲያን ልባቸውን ከመስጠት ይዘገያሉ፡፡ ወጣቶች ወደ አገልግሎት እንዳይገቡ እንቅፋት ከሚሆኑ ነገሮች መካከል አንዱ ቤተ ክርስቲያንን አለማወቅ ነው፡፡

፩. ቤተ ክርስቲያንን አለማወቅ፡- ብዙ ወጣቶች ለስብከተ ወንጌል ልብ ሰጥቶ ከመታደም፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ጊዜ ሰጥቶ በተመስጦና በጥልቀት አንብቦ ከመረዳት፣ መምህራነ ወንጌልን፣ ሊቃውንትንና ካህናትን ቀርቦ ከመጠየቅ ይልቅ በተለያየ ሰበብና ምክንያት ራሳቸውን ስላሸሹ ቤተ ክርስቲያንን በውል ማወቅ፣ መረዳት ሲከብዳቸው ይስተዋላል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እናውቃለን ብለው የሚያስቡት እንኳን ዓለም ከምታቀርብላቸው ሥጋዊ ፍላጎትን ከሚያነሣሱ፣ ከማኅበራዊ የትስስር ገጾች ባለቃቀሟቸውና በቃረሟቸው የተቆራረጡና ምሉእ ያልሆኑ ሕጸጽና ግድፈት ከበዛባቸው መረጃዎች ተመስርተው ስለሆነ ቤተ ክርስቲያንንና ሐዋርያዊ ተልኮዋን በውል ተረድተዋል ለማለት ይቸግራል፡፡

ብዙኃኑ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን ምንድን ናት? ተልዕኮዋስ ምንድን ነው?  ቤተ ክርስቲያን ከእኔ ምን ትፈልጋለች? እኔስ ከቤተ ክርስቲያን የማገኘው ጥቅም ምንድን ነው? እነዚህን ለመሰሉ መሠረታዊ ጥያቄዎች ለኅሊናቸው በውል ምላሽ መስጠት ሲቸግራቸው ይስተዋላል፡፡ ለአንዳድ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን አቡነ አገሌ፣ አባ እገሌ፣ ሰባኪ/ዘማሪ እገሌ ናቸው። እነዚህ ዓይኑንና ተስፋውን የጣለባቸው ሰዎች ፈተና አድክሟቸው የዓለም አንጸባራቂ ውበት ስቦ፣ አታልሏቸው እንደ ዴማስ (፪ጢሞ. ፬፥፲) ወደ ኋላ መጓዝ፣ መሰናከል፣ በጀመሩ ጊዜ ቀድሞውኑ ቤተ ክርስቲያንን በእነዚህ ሰዎች ትከሻ ላይ ወስነዋት ነበርና የእነሱን ድካምና ጥፋት ከቤተ ክርስቲያን ለይቶ ማየት ያቅታቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ከሕይወት መንገድ ተደናቅፈው ይወድቃሉ፡፡

ለዚህም ነው በየአድባራቱ፣ ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶች “የእገሌ መዝሙር ካልተዘመረ፣ እገሌ የተባለ ሰባኪ ካልመጣ፣ አባ እገሌ ካልተሾሙ፣ አቡነ እገሌ ካልተሻሩ አላገለግልም፣ አልመጣም” ወዘተ በማለት ቀስ በቀስ ከቤተ ክርስቲያን እቅፍ የወጡና እየወጡ ያሉ ምእመናን ቁጥራቸው እየበዛ የመጣው። ነገር ግን በእውነት ያለ ሐሰት ቤተ ክርስቲያን ከነዚህ ሁሉ ነገሮች በላይ የሆነች አንዲት፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኩላዊት (ዓለም አቀፋዊት) ናት፡፡ (ሊቀ ጉባኤ አባ አብራ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት)። ለዚህም ነው አበው በሃይማኖት ጸሎት ደግመን ደጋግመን እንዘክረው ዘንድ “ከሁሉ በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን” ብለው ያስቀመጡልን።

ቤተ ክርስቲያንን አለማወቅ በሦስት ክፍሎች ከፍለን ልናየው እንችላለን፡፡

የመጀመሪያው ስለ ቤተ ክርስቲያን ምንም ዓይነት ዕውቀትና ግንዛቤ አለመኖር ነው፡፡ አንዳንድ ወጣቶች ወላጆቻቸው በልጅነታቸው ካመላለሷቸው በኋላ እግሮቻቸው ደጀ ሰላም አልረገጡም፡፡ ነገር ግን በአንገታቸው ማዕተብ አጥልቀው፣ በስማቸውም ክርስቲያን የክርስቶስ ወገን ተሰኝተዋል፡፡ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ቤተ ክርስቲያን ምን እንደሆነች፣ ተልእኮዋ ምን እንደሆነ፣ በዚህ ወቅት ቤተ ክርስቲያን ምን ሁኔታ ላይ እንደሆነች አያውቁም፤ የማወቅ ፍላጎታቸውም የደከመ ነው፡፡ እናም መቼም ቢሆን ውስጣቸው በቤቱ ቅናት ተቃጥሎ “እስመ ቅንዐተ ቤትከ በልዐኒ፤ የቤትህ ቅንዓት በልቶኛልና” (መዝ.፷፰፥፱)  ብለው ለአገልግሎት ይነሡ ዘንድ፣ የሀገር፣ የቤተ ክርስቲያን መጥፋት አሳዝኗቸው ወደ መንፈሳዊ ቁጭት ውስጥ ይገቡ ዘንድ ኢታርእየነ ሙስናሃ፣ ለኢየሩሳሌም የኢየሩሳሌምን ጥፋት አታሳየን ሊሉ አይችሉም፡፡

በሁለተኛ ደረጃ ቤተ ክርስቲያንን (አስተምህሮዋን፣ ዶግማና ቀኖናዋን) በግል ምልከታቸው በሥጋዊ ድካማቸው ደረጃ ዝቅ አድርገው “ምን አለበት፣ ምን ችግር አለው፣ ብዙ ባናካብድ” በሚሉ ሰበቦች ታስረው ቤተ ክርስቲያንን ያወቁ የሚመስላቸው ነግር ግን ያላወቁ ወጣቶች ናቸው፡፡ ለእነዚህ ዓይነቶቹ ምእመናን ቤተ ክርስቲያን  የምታስፈልጋቸው ሥጋዊ ፈተናዎች ( ሥራ ማጣት፣ ከወዳጃቸው ጋር መጋጨት፣ የሥጋዊ ደዌ፣ ሕመም፣ የኑሮ መክበድ፣ የትምህርት ጉዳይ) ሲያስጨንቃቸው ብቻ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን የሰማያዊና ዘለዓለማዊ ሕይወት ሰጭነት፣ የቤተ ክርስቲያን የነፍስ መጋቢነት አይታያቸውም፡፡

ሩጫቸው ምድራዊ ስኬት እስከ ማግኘትና መጎናጸፍ ብቻ ነው፡፡ እርግጥ ነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እናንተ ደካሞች፣ ሸክማቹሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ” (ማቴ.፲፩፥፳፰) ሲል እንዳስተማረን በድካማችን ጊዜ እግዚአብሔርን መጥራት በችግራችን ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን ደጅ መጥናት በጎና ተገቢ ተግባር ነው፡፡ ነገር ግን  የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ አሳስቧቸው ሳይሆን ለአገልግሎት የሚመጡት ለሥጋዊ ዓላማ ብቻ ነውና ያ ጥያቄቸው መልስ ሲያገኝ (ሥራ ወይም ትዳር ሲይዙ) ከወላጆቻቸው ቤት ብቻ ሳይሆን ከቤተ ክርስቲያንም ይኮበልላሉ፡፡

በሦስተኛ ደረጃ ቤተ ክርስቲያንን ባልተረጋገጠና በተምታታ መረጃ በአላዋቂዎች ትምህርት ተመርኩዘው እናውቃለን የሚሉት ናቸው፡፡ በዚህኛው የዕውቀት ደረጃ ብዙ ወጣት ምእመናን ቤተ ክርስቲያን ለዘመናዊነት፣ ሠርቶ ለመለወጥ፣ ራስን ለማሳደግ ጠላት አድርገው ይስሏታል። መንፈሳዊነትንና ለቤተ ክርስቲያን አሳቢነትን ራስን ካለመንከባከብ፣ ንጽሕናን ካለመጠበቅ እና ሥራና ትምህርትን እርግፍ አድርጎ ትቶ የብሕትውናን ኑሮ ከመኖር ጋር የሚያዛምዱ ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች በሕይወታቸው ውስጥ እግዚአብሔርን በፈራጅነቱ በቀጭነቱ ፈርተው ያመልኩታል እንጂ  ከፍቅር የመነጨ ፈሪሃ እግዚአብሔር አይኖራቸውም፡፡ የእንደዚህ ዓይነት ሰዎች ሌላው መለያ ባሕርያቸው በመንፈሳዊ መንገዳቸው ፊት ለፊት የሚታያቸው የክርስቶስ ሕይወት፣ አልያም የአበው ቅዱሳን ተጋድሎ አይደለም፡፡ ከዚያ ይልቅ በቅርብ የሚያገኙትን አገልጋይ የፍጹምነት ምሳሌ አድርገው ይስሉታል፡፡ እነዚህ ወጣቶች ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ እነዚህን ሰዎች ከማምለክ ባልተናነሰ ሲያደምጡ ይስተዋላል፡፡ በአጠቃላይ ሦስቱም ትክክለኛ መንገዶች አይደሉም፡፡

.አልችልም/”አይገባኝም” ማለት ትሕትናና ራስን ዝቅ ማድረግ፡- ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው በተግባር ሠርቶ፣ በቃል አብራርቶ፣ በምሳሌ አጉልቶ ያስተማረን፣ አባቶቻችን በመንፈሳዊ ክብር ከፍ ከፍ ያሉበት ታላቅ ጸጋ ነው፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱሳት መጻሕፍት ደግመው ደጋግመው ስለ ትሕትናና ራስን ዝቅ ስለማድረግ በአጽንዖት የሚነግሩን “ትሕትናና  እግዚአብሔርን መፍራት ባለጠግነት፣ ክብር፣ ሕይወትም ነው”  እንዲል(ምሳ.፳፪፥፬)፡፡ በመንፈሳዊ አገልግሎት ራስን ዝቅ አድርጎ ቅድሚያ ለሌሎች መስጠት የተገባ እንደሆነ ብርሃነ ዓለም ቅዱሰ ጳውሎስ “እያንዳንዱ ባልንጀራው ከርሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቁጠር”  (ፊልጵ.፪፥፫) ሲል ይነግረናል፡፡

ነገር ግን ትሕትናችን፣ ራስን ዝቅ ማድረጋችን ለእታይ እታይ ባይነትና ከንቱ ውዳሴ ሰለባ ከሆነ፣ በልቦናችን አንዳች የትሕትና ፍሬ ሳይኖር ውስጣችን በትዕቢት ወደ ላይ ተወጥሮ ውጫዊ አካላችን ለብቻው የሚያጎነብስ ከሆነ፣ ትሕትናችን ለምድራዊ ክብር መሻት፣ ዓለማዊ ሀብትን በማየት አለዚያም ራስችንን ከኃላፊነት፣ ከአግልግሎትና መታዘዝ ለማሸሽ የመደበቂያ ምሽግ ሆኖ ካገለገለ በውኑ ይህንን በቅዱሳት መጻሕፍት ሚዛንነት ትሕትና ነው ማለት አይቻልም፡፡ በዘመናችን ብዙ ወጣቶች ወደ ቤተ ክርስቲያን ቀርበው፣ በአገልግሎት ተሳትፈው የበረከት ተቋዳሽ እንዳይሆኑ ትልቅ እንቅፋት እየሆነባቸው ያለ ጉዳይ ትሕትናን የሚመስል ነገር ግን ትሕትና ያልሆነ ያልችልም ባይነት ስሜት፣ ራስን ዝቅ በማድረግ የተደበቀ ከኃላፊነትና ከአገልግሎት የመሸሽ ልማድ ነው፡፡

የሰው ልጅ በአስተሳሰቡና በአመለካከቱ አልችልም፣ ደካማ ነኝ የሚል ስሜት ካሳደረ፤ የእግዚአብሔርን ረዳትነት ተማምኖ “ወደ እርሱ ቅረቡ ያበራላችሁማል፣     ፊታችሁም አያፍርም” (መዝ.፴፫፥፭) እንዲል መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት ወደ ቤተ ክርስቲያን ቀርቦ ለተግባር፣ ለድርጊት መቸም ቢሆን ውስጣዊ መነሣሣትና ቁርጠኝነት አይኖረውም፡፡ ሰው የሚያስበውን ያንኑ ይመስላል እንዲል አስተሳሰባችን ከተግባራችን ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ይህ የአስተሳሰብ ደካማነት፣ እምነተ ጎደሎነት ወይም የጥርጥር መንፈስ ተብሎ ይገለጻል፡፡ በውኃ ላይ መራመድን ሽቶ በመሐል በመጠራጠሩ ሊሰምጥ የነበረውን ቅዱስ ጴጥሮስን ማሰብ ያሰፈልጋል፡፡ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ በጥብዓት ከተጓዘ በኋላ በመሐከል ግን የጥርጥር መንፈስ ወደ እርሱ እንደገባና እምነተ ጎደሎ በመሆኑ እንደተገሠጸ ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል (ማቴ. ፲፬፥፳፬)፡፡

በእርግጥ አበው ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ሊቃውንት፣ ጻድቃን ሰማዕታት ለታላቅ አገልግሎትና ተልእኮ ከፈጣሪ ጥሪ ሲደረግላቸው ከልብ በመነጨ መንፈሳዊ ትሕትና ይህንን ጥሪ እቀበል ዘንድ እኔ ማን ነኝ፤ ይህንን ተልእኮስ እቀበል ዘንድ እኔ ምንድን ነኝ ፤ እኔ ደካማ ሰው ነኝ ሲሉ የተሰጣቸው ተልእኮ ታላቅነትን፣ የእነርሱን ደካማነት አሳይተዋል፡፡ ነገር ግን ይህንን ብለው ከኃላፊነትና ከአገልግሎት አልሸሹም ይልቅ ሰማያዊ ተልእኳቸውን በትጋትና በብቃት ተወጡ እንጂ፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሕዝበ እስራኤልን ከፈርዖን ግፍና ባርነት ነጻ ያወጣ ዘንድ መመረጡን በሰማበት በዚያች ቅጽበት “እኔ ኮልታፋ ምላሴም ጸያፍ የሆነ ሰው ነኝ ትናንት ከትናንት ወዲያ ባርያህንም ከተናገርከኝ ጀምሮ አፈ ትብ ሰው አይደለሁምን” (ዘጸ. ፬፥፲) በማለት የእርሱን ደካማነት የተሰጠውን አደራና ኃላፊነት ታላቅ መሆን ይገልጻል። ነገር ግን የሙሴ ትሕትና ልባዊ ነበርና፤ “ሙሴም በምድር ላይ ካሉት ሰዎች ሁሉ ይልቅ እጅግ ትሑት ነበር” (ዘኊ.፲፪፥፫) እንዲል፡፡ ይህንን ማለቱ ተልእኮውን ከመወጣት አላስቀረውም፡፡

ከሁሉም በላይ ብዙ ወጣቶች እኔ ገና ጀማሪ ነኝ፣ እኔ ምንም አልጠቅምም፣ እኔ ለቤተ ክርስትያን የምሆን ሰው አይደለሁም ሲሉ ለሰውም ለራሳቸው ኅሊናም እየነገሩ በትሕትና ሰበብ በቅድሚያ ከአገልጋይነት እየቆዩም ከጾም ጸሎት ሸሽተው የጠፉ ሰዎች ብዙዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ አንድ አገልጋይ “ሁልጊዜም ስደክም ያን ጊዜ ኃይለኛ ነኝ“ (፪ኛቆ፲፪፥፲) በማለት ሐዋርያው እንዳስተማረን እርሱም ለበለጠ ትጋት፣ ለበለጠ አገልግሎት መነሣሣት ይገባዋል። ምክንያቱም በእግዚአብሔር ቤት ታናሽና ታላቅ ኃላፊነት ያለበትና የሌለበት ሰው የለም አምላካችን በሁላችንም ደጅ ቁሞ “እነሆ በደጅ ቁሜ አንኳኳለሁ ማንም ድምፄን ቢሰማ ደጁንም ቢከፍትልኝ ወደርሱ እገባልሁ ከእርሱም ጋር እራት እበላለሁ እርሱም ከእኔ ጋር ይበላል” (ራዕ ፫፥፳) እያለ ለበረከት ይጠራናልና፡፡ ስለዚህ እያንዳንዳችን ይህን ጥሪ አክብረን የሚጠበቅብንን ተወጥተን የስሙ ቀዳሽ የመንግሥቱ ወራሽ እንድንሆን ልንተጋ ይገባል፡፡ ለዚህም እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ ይቆየን፡፡

ምንጭ፡- ከሐመር መጽሔት ሰኔ (ሰኔ ፳፻፲፩ ዓ.ም)

“ያድነን ዘንድ ተነሥተህ አምላክህን ጥራ”(ዮና.፩፥6)

በእንዳለ ደምስስ

እግዚአብሔር በአርአያውና በአምሳሉ ከሌሎች ፍጥረታት አልቆ የፈጠረው የሰው ልጅ የተሠራለትን ሕግና ትእዛዝ በማፍረስ፣ ለእርሱ የተሻለውን፣ የተሰጠውን ትቶ የተከለከለውን በማድረጉ ወደቀ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የእጁ ሥራ የሆነው የሰው ልጅ(አዳም)  ቢበድልም ዝም ብሎ አልተወውም፡፡ አዳም ንስሓ በገባ ጊዜ እግዚአብሔር የአዳምን ከልብ የመነጨ ጸጸትና ልቅሶ ተመልክቶ ራራለት፡፡ “አምስት ቀን ተኲል ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ”(ቀሌ.፫፥፲፰-፲9) በማለት ስለ ፍጹም ፍቅሩ ቃል ኪዳን ገባለት፡፡

የሰው ልጅ በደሉ እጅግ አስከፊ ቢሆንም ንስሓ ይገባ ዘንድ እግዚአብሔር በትዕግሥት ይጠብቃል፡፡ ከዚህም አልፎ ይታዘዙለት ዘንድ የመረጣቸውን የእግዚአብሔር ሰዎችን እያስነሣ በእነርሱ ላይ አድሮ በመገሰጽ ወደ ቀናው መንገድ ይመለሱ ዘንድ ያደርጋል፡፡ ነገር ግን ከአዳም ጀምሮ የሰው ልጅ ያልበደለበት ጊዜ የለም፡፡ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በበዛ ቁጥር ደግሞ የሰው ልጆች በደልም እጅግ እየከፋ በመሄዱ እግዚአብሔር ሰውን በመፍጠሩ እሰከመጸጸት እንዳደረሰው መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ “እግዚአብሔርም የሰዎችን ክፉ ሥራ በምድር ላይ እንደበዛ የልባቸው ሐሳብ ምኞትም ሁል ጊዜ ፈጽሞ ክፉ እንደሆነ አየ፡፡ እግዚአብሔርም ሰውን በምድር ላይ በመፍጠሩ ተጸጸተ”(ዘፍ.6፥፭-6) እንዲል፡፡

በየዘመናቱ የሰዎች ኃጢአት እየከፋ፣ ከኃጢአታቸው ይመለሱ ዘንድ እግዚአብሔር ነቢያትን፣ ሐዋርያትን፣ ሊቃውንቱንና መምህራኑን ቢያስነሣም፣ እግዚአብሔርን በመፈታተናቸው ትዕግሥቱንም በማሳጣት ተቀስፈዋል፤ ምድር ተከፍታም ውጣቸዋለች፣ ለጠላቶቻቸውም አሳልፎ ሰጥቷቸዋል፡፡ “የኃጢአት ትርፍዋ ሞት ነውና” እንዲል(ሮሜ.6፥፳፫)፡፡ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ያስገዙና እንደ ቃሉም የሚጓዙ ቅዱሳን እንዳሉ ሁሉ፣ ለጥፋት የሚፋጠኑ፣ ምድሪቱንም የሚያስጨንቁ ተነሥተው ያውቃሉ (የነነዌ ሰዎች)፡፡

እግዚአብሔር በየዘመናቱ ሰዎችን እያስነሣ በቅዱሳን አድሮ እየገሰጸ መንገዳቸውን እንዲያቀኑ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ እንዲመለሱ ያደርጋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ በነበረበት ዘመን እግዚአብሔር የሰዎችን ክፋት ተመልከቶ ነቢዩ አሳይያስን ይልከው ዘንድ ተገልጦለታል፡፡ መልአኩንም ልኮ አፉን በፍም ዳሰሰው፣ ኃጢአቱም ተወገደለት፡፡ “ማንን እልካለሁ? ማንስ ወደዚያ ሕዝብ ይሄድልናል? ሲል ሰማሁ፤ እኔም እነሆኝ ጌታዬ እኔን ላከኝ” አልሁ፡፡ በማለት ለእግዚአብሔር በቅንነት እንደታዘዘ እንመለከታለን፡፡ (ኢሳ.6፥6-9)፡፡

ነቢዩ ዮናስ ግን የነነዌ ሕዝብን በደል የተመለከተው እግዚአብሔር ሕዝቡን ይገስጽ ዘንድ በላከው ጊዜ ግን የነነዌ ሰዎችን ከበደላቸው ይመለሱና ንስሓ ይገቡ ዘንድ እንዲሰብክ(እንዲናገር) ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ትእዛዝ በመጣስ ሽሽቷል፡፡ ምክንያቱም የነነዌ ሰዎች ክፋት መብዛት፣ ልባቸው እንደደነደነና ለጩኸቱ ሁሉ በጎ ምላሽ እንደማይሰጡት በሰው ሰውኛ አስተሳሰብ በራሱ መዝኖ አይሳካልኝም በሚል ከእግዚአብሔር ይልቅ ሰዎቹን ፈርቶ ሽሽትን ምርጫው አደረገ፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ማድረግ እንደሚችል ዘነጋ፡፡ “ያለ እኔ ምንም ማድረግ አትችሉምና” በማለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተናገረ(ዮሐ.፲፥፭)፡፡ በራሱ ሐሳብና ፍላጎት ተመርቶ ከእግዚአብሔር ሸሽቶ ያመለጠ የለም፡፡ ዮናስ ይህንን እውነታ ባለመገንዘብ የነነዌ ሕዝብ ልቡ የደነደነ ነው፣ እኔ ብናገርም የሚሰማኝ የለም፣ አያምኑኝም በማለት ከእግዚአብሔር ያመለጠ መስሎት ወደ ተርሴስ ኮብልሏል፡፡

ብዙዎቻችን እግዚአብሔር የሚለንን ትተን በራሳችን ስሜትና ፍላጎት ተመርተን ኃጢአትን እንሠራለን፡፡ ለኃጢአታችን ሥርየትን ከመፈለግና ወደ እግዚአብሔር ከመጮህ ይልቅ ሰበብ እየፈለግን ያደረግነውን ክፉ ነገር ለመሰወር እንሯሯጣለን፡፡ የማይገለጥ የተሰወረ፣ የማይታይ የተሸሸገ የለምና” አንዲል (ሉቃ.፲፪፥፪)፡፡ ከእግዚአብሔር ሸሽተን የት እንደርሳለን? ትእዛዙን ተላልፈንስ መጨረሻችን ምን ሊሆን ነው? ዮናስ የእግዚአብሔርን ድምጽ ከመስማትና ከመፈጸም ይልቅ ለራሱ ክብር ተጨነቀ፡፡ መኮብለል ምርጫው ሆነ፡፡

በእርግጥ የዮናስ ጭንቀት ሕዝቡም ከመበደል፣ እግዚአብሔርም ምሕረት ከማድረግ አይመለሱም፣ ተናግሬ ውሸታም ከምባል መኮብልል ይሻለኛል በሚል ከንቱ ሐሳብ ተመርቶ ተጓዘ፣ ግራና ቀኛቸውን ለይተው ስለማያውቁ ሕፃናትና እንስሳት ማሰብ ተሳነው፡፡ ወደ ተርሴስም ለመሄድ በመርከብ ተሳፈረ፡፡

ዮናስ ከእግዚአብሔር ያመለጠ መስሎት ቢሄድም ያጋጠመው ነገር ግን ከባድ መከራ ነው፡፡ ተሳፈሪዎችንና ዮናስን ለመታደግ እግዚአብሔር ብዙ ዕድሎችን ለዮናስ ሰጥቶት ነበር ነገር ግን በመርከቡ ታችኛው ክፍል ገብቶ፣ ሐሳቡን ጥሎ እንቅልፍ ተኛ፡፡  ዐውሎ ነፋስም ተቀሰቀሰ፡፡ የመርከቡ አለቃና ተጓዦችም ተጨንቀው ዮናስን ከተኛበት በማስነሣት “ምነው ተኝተሃል? እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ያድነን ዘንድ ተነሥተህ አምላክህን ጥራ” አሉት፡፡ ዕጣም ተጣጣሉ፣ ዕጣው በዮናስ ላይም ወደቀ፡፡

ከእግዚአብሔር ትእዛዝና ጥሪ አፈንግጦ ኮብልሏልና ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንደደረሰባቸው የተረዳው ዮናስ “ይህ ታላቅ ማዕበል በእኔ ምክንያት እንዳገኛችሁ አውቃለሁና አንሥታችሁ ወደ ባሕሩ ጣሉኝ” አላቸው፡፡ ዮናስ ዘግይቶም ቢሆን እግዚአብሔርን እንደበደለ፣ ከእርሱም ማምለጥ እንደማይቻል ሲረዳ በራሱ ላይ ፈረደ፡፡ ወደ ባሕሩም ጣሉት፡፡ እግዚአብሔርም ይሞት ዘንድ ፈቃዱ አይደለምና ዓሣ አንበሪ ሆድ ውስጥ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት አሳድሮታል፡፡ በመጨረሻም ነነዌ ላይ ዓሣ አንበሪው እንዲተፋው አደረገ፡፡ (ዮና.፩)፡፡

ነቢዩ ዮናስ የታዘዘውን ለመፈጸም ወደ ነነዌ ገብቶም ሕዝቡ ወደ እግዚአብሔር እንዲመለስ፣ ከእንስሳቱና ከሚያጠቡ ሕፃናት ጀምሮ ለሦስት ቀናት በዋይታና በልቅሶ፣ በጾምና ጸሎት እንዲቆዩ ሰበከ፡፡ ከሰማይ ወርዶ ከሚበላቸው እሳት ዳኑ፡፡ በሦስት ቀናት ጾምና ጸሎት እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደታደገ እኛም በደላችንን እያሰብን፣ በጸጸትና በንስሓ ሆነን እግዚአብሔርን ብንለምን የለመንነው ሁሉ ይከናወንልናል፡፡ ዘመናችን እጅግ አስከፊ ነገሮች የምንሰማበት ጊዜ ቢሆንም ከኃጢአተኞች ጋር ከመተባበር ይልቅ ወደ እግዚአብሔር በተሰበረ ልብ መመልስ ይሻለናል፡፡ የነነዌ ሰዎችን ከኃጢአት እስራት ፈትቶ እንዳዳናቸው እኛንም ያድነናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ከፊት ይልቅ ትጉ”(፪ኛ ጴጥ.፩፥፲)

በቀሲስ ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

የወጣትነት የዕድሜ ክልል ብርቱ አቅማችን ተጠቅመን ከሌላው ጊዜ በተሻለ ብዙ ሥራ የምንሠራበት ወቅት  ነው፡፡  ትጋት  ለክርስቲያናዊ ሕይወት አስፈላጊ ነው፡፡  ምክንያቱም በክርስትና እምነታችን ዕለት ዕለት በጎ ተግባራትንና ትሩፋትን በመሥራት ኑኖአችን እግዚአብሔርን ማክበር ስለሚገባ ነው፡፡

በተለይም የወጣትነት ዕድሜ ክልል አብዝቶ በመጋደል መንፈሳዊ  ሩጫችንን ለማፋጠን አመቺ  ነው፡፡  በዚያው ልክ  ደግሞ  በወጣትነት ጊዜ  በራስ ሕዋሳት  መፈተንና  መጥፎ የሆነ ስሜታዊነት የሚያይልበት ወቅት ስለሆነ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ  ነፍስ  በማስገዛት በሕገ   እግዚአብሔር   ተገዝቶ   መኖር   ያስልጋል፡፡ ይህ   ለሕገ እግዚአብሔር መገዛት ለሁሉም ነው፡፡ ማለትም ሕፃን፣ ወጣት፣ ሽማግሌ የማይል መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ ነገር ግን ወጣትነት ከላይ የጠቀስናቸው ፈተናዎች የሚበረቱበት  ስለሆነ ለይተን አቀረብን እንጂ፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ  ጴጥሮስ  “ከፊት  ይልቅ  ትጉ”  ብሎ  ምክሩን  የለገሰበትን ምክንያት ዘርዝሮታል፡፡ እነሱም ለመረዳት መልእክቱን ቃል በቃል መመልከተ አስፈላጊ ነው፡፡

“እናንተ ግን በሥራ ሁሉ እየተጋችሁ በእምነት በጎነትን፣ በበጎነትም ዕውቀትን፣ ጨምሩ፣ በዕውቀትም ንጽሕናን፣ በንጽሕናም ትዕግሥትን፣ በትዕግሥትም እግዚአብሔርን ማምለክን እግዚአብሔርን በማምለክ ወንድማማችነትን፣ በወንድማማችነት ፍቅርን ጨምሩ እነዚህ ነገሮች ለእናንተ ሆነው ቢበዙ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በማወቅ ሥራ ፈቶችና ፍሬ ቢሶች እንዳትሆኑ ያደርጓችኋልና፡፡ እነዚህ ነገሮች የሌሉት ዕውር ነውና በቅርብ ያለውን ብቻ ያያል የቀደመውንም የኃጢአቱን መንጻት ረስቷል፡፡ ስለዚህ ወንድሞች ሆይ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታጸኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉም፡፡ እንዲሁ ወደ ዘለዓለሙ ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት መግባት በምልዐት ይሰጣችኋል” (፪ኛጴጥ.፩፥፭-፲፭) በማለት ሰፋ አድርጎ በመንፈሳዊ ሕይወታቸን በአገልግሎት እንተጋ ዘንድ ያስፈለገበትን ምክንያት ዘርዝሮታል፡፡

በመሆኑም ከላይ የተነሣንበትን ኃይለ ቃል ስንመለከት “እናንተ ግን በሥራ ሁሉ እየተጋችሁ “የሚል ነው፡፡ በሥራ ሁሉ ሲል መንፈሳዊ በሆነ ሥራ (አገልግሎት) መሳተፍን ይጠቁማል፡፡ ይህም መንፈሳዊ ሥራ ወይም አገልግሎት እንደተሰጠን ጸጋ መጠን የሚገለጥ ነው፡፡ የፀጋ ሥጦታ ልዩ ልዩ እንደሆነ አውቀን በተቀመጥንበት የአገልግሎት መስክ ለአእምሮ የሚመቸውን አገልግሎት  መፈጸም  ነው፡፡  ምንም  እንኳ  ወጣቶች  በውርዝውና  ዕድሜ  ላይ  እያለን ሕዋሳቶቻችን ፈቃደ ሥጋን ለመፈጸም የሚፈልጉበትወቅት  ቢሆንም  በዚህ ውብ በሆነና ለአገልግሎት ስኬት   አመቺ   በሆነው ወጣትነታችን   ሰውነታችን ለእግዚአብሔር ክብር (አገልግሎት) እንዲውል ማድረግ እጅግ ማስተዋል ነው፡፡ ለዚህም ነው፤ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ   ለሮሜ   ክርስቲያኖች   በላከላቸው   መልእከቱ   “ወንድሞቻችን   ሰውነታችሁን ለእግዚአብሔር ሕያውና ቅዱስ ደስ የሚያሰኝም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኀራኄ እማልዳችኋለሁ፡፡ ይህም በዕውቀት የሚሆን አገልግሎታችሁ ነው፡፡ ይህን ዓለም አትምሰሉ ልባችሁንም አድሱ እግዚአብሔር የሚወደውን መልካሙንና እውነቱን መርምሩ (ሮሜ. ፲፪፥፩) እንዲል፡፡

ሐዋርያው እንደመሰከረው ሰውነትን ቅዱስና ሕያው ደስም የሚያሰኝ መሥዋዕት አድርጎ ማቅረብ ማለት እግዚአብሔር ራሱን በገለጠልን መጠን ስለ እርሱ ማወቅ ነው፡፡ ይህም በእምነት ሆነን እግዚአብሔር እኛ ከምናውቀው ከዕውቀታችን በላይ (ከአእምሮ በላይ) ምጡቅ ባሕርይው የማይመረመርና ማንም ሊደርስበት የማይችል መሆኑን ተረድተን ባወቅነው ልክ እንደ አቅማችን እሱን የምናገለግልበት አገልግሎት ነው፡፡ እሱም ሁሉም እንደ አቅሙ በተለያየ ፀጋ እግዚአብሔርን እንዲያገልግል ተጠርቷል፡፡

ይህው ሐዋርያ በጻፈው መልእክቱ “በተሰጠኝ በእግዚአብሔር ፀጋ ሁላችሁም እንዳትታበዩ እነግራችኋለሁ ራሳችሁን ከዝሙት የምታነጹበትን አስቡ እንጂ በትዕቢት አታስቡ ሁሉም እንደ እምነቱ መጠን እግዚአብሔር እንዳለው ይኑር፡፡ በአንዱ ሰውነታችን ብዙ የአካል ክፍሎች እንዳሉ ሥራውም ልዩ ልዩ እንደሆነ እንዲሁ ሁላችንም ብዙዎች ስንሆን በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ አካል ነን፡፡ እርስ በእርሳችን እያንዳንዳችን የሌላው አካሎች ነን፡፡ ስጦታውም ልዩ ልዩ ነው፡፡ እግዚአብሔርም በሰጠን ፀጋ መጠን ልዩ ልዩ ስጦታ አለን፡፡ ትንቢት የሚናገር  እንደ እምነቱ መጠን ይናገር የሚያገለግልም በማገልገሉ ይትጋ የሚያስተምርም በማስተማሩ ይትጋ የሚመክርም  በመምከሩ  ይትጋ  የሚሰጥ  በልግስና  ይስጥ  የሚገዛም  በትጋት  ይግዛ የሚመጸውትም በደስታ ይመጽውት (ሮሜ.፲፪፥፫) በማለት ሁሉም በተሰጠው ፀጋ ሊተጋ እንደሚገባ ያስረዳል፡፡

በመሆኑም የወጣትነት ጊዜ በአገለግሎት አብልጠን የምንተጋበት ወቅት ነው፡፡ ምክንያቱም ወጣትነት ጉልበቱ፣ ዕውቀቱ፣ ችግርን ተቋቁሞ ማለፍና በመሰደድም ሆነ  በብዙ  ሮጦ ማገልገል የሚቻልበት ስለሆነ ነው፡፡ ስለዚህ ልዩ ልዩ በሆነ ፀጋ ሥጦታ እግዚአብሔር እያንዳንዳችን ሾሞናል፡፡ ይህንንም ፀጋ ያገኘነው ከእርሱ በተወለድንበት ዳግም ልደት ነው፡፡

ከእርሱ ከተወለድን ዘንድ ደግሞ የእርሱ ፀጋ በእኛ ላይ አለ፡፡ ያን የጸጋ ስጦታችንን በትጋት እንድንፈጽም ያስፈልጋል፡፡ በወጣትነትም ጸጋ እግዚአብሔር በዝቶአልን ከሌላው ጊዜ በተሻለ የምናገለግልበት ወቅት በመሆኑ ራሳችንን ለቃሉ ማስገዛት ያስፈልጋል፡፡ ትጋታችንም ከሌላው ጊዜ በተሻለ ሊሆን ይገባል፡፡ ምክንያቱም ወጣትነት የሕይወታችን ዋነኛው ክፍል ስለሆነ በመንፈሳዊ ሕይወት ልንጠነክር ይገባል፡፡

ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ መግቢያ እንደተመለከትነው “እናንተ ግን በሥራው ሁሉ እየተጋችሁ” በማለት ማድረግ የሚገባንን ነገር በመጥቀስ ሲዘረዝር በመጀመሪያ በእምነት በጎነትን ጨምሩ ይላል፡፡

“በእምነት ጎነትን ጨምሩ”

እምነት የሁሉ መሠረት እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ይሁን እንጂ እምነት በጎነት ሊጨምርበት ይገባል፡፡ ለዚህም ነው አብርሃም በእግዚአብሔር አምኖ በቤቱ በበጎነት እንግዶችን በመቀበል  የተራቡትን  የተጠሙትን  በመመገብ  እምነቱነ  በበጎ  ሥራ  ይገልጥ  የነበረው እምነቱም  ጽድቅ  ሆኖ  ተቆጠረለት  እንዳለው  እምነታችን  የሚታወቀው  በበጎነት  ሥራ ሲገለጥ ነው፡፡ እርሱም የመጀመሪያ የበጎ ሥራ መጀመሪያ ለእግዚአብሔር መታዘዝ ነው፡፡ “አብርሃም በእግዚአብሔር አመነ እምነቱም ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረለት (ገላ.፫፥፮) እንዲል፡፡

አብርሃም እግዚአብሔርን አምኖ ከሀገሩ ከዘመዶቹ ከቤተሰቡ መካከል ተለይቶ መውጣቱ በእግዚአብሔር መታመኑ (ማመኑ) ነው፡፡ በጎነትንም ለማሳየት የቻለው በእምነቱ ስለሆነ በእምነቱ በጎነትን ጨመረ፡፡ እኛም በእምነታችን ላይ በጎነትን ችግረኛ መርዳትን ድሆችን መመገብን  ለሰው  በጎ  ነገር  ማድረግን  ልናበዛ  ይገባል፡፡  “መልካም  ሥራ  ለራስ  ነው” እንደሚባለው ሁሉ እግዚአብሔርን የምናይበት እመነታችን(ሃይማኖታችን)   በበጎነታችን በምንሠራው መልካም ሥራ ሊገለጥ ወይም ሊታይ ያስፈልጋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳስተማረን ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ከትናንትና ይልቅ ዛሬ ላይ በትጋት በምንፈጽመው አገልግሎት ማደግ ይኖርበታል የዛሬ ትጋታችንም እንዲሁ ጨምሮ እግዚአብሔር ቢፈቅድ መንፈሳዊ ፍሬአችን የተሻለ ሆኖ መታየት ይኖርበታልና በሁሉ ነገር መትጋት አለብን፡፡ አምላከ ቅዱሳን ልዑል እግዚአብሔር ትጋቱን ማስተዋሉን ለሁላችን ያድለን

አሜን፡፡ ይቆየን..