በዓለ ጰራቅሊጦስ

በዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ

በዓለ ጰራቅሊጦስ ከዘጠኙ የጌታችን ዓበይት በዓላት አንዱ ሲሆን መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የወረደበትን ቀን የምናስብበት በዓል ነው። ጰራቅሊጦስ ማለት ከአብ እና ከወልድ ጋር ለምንሰግድለት የዘለዓለም አምላክ ለሆነው ለሚያነጻ፣ ሊሚያጽናና እና ለሚቀድስ ለመንፈስ ቅዱስ የመጠሪያ ስም ነው፡፡ በዚህም በዓለ መንፈስ ቅዱስ ለማለት በዓለ ጰራቅሊጦስ ብለን እንጠራዋለን፡፡

ይህ ታላቅ በዓል የሐዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችበት ቀን ነው፡፡ ይህም ስለ ምነው ቢሉ ቤተ ክርስቲያን ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በየዘመኑ በተነሡ ገዢዎችና እናውቃለን፣ እንመራመራለን በሚሉ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን በሚያደርሱት አድርገው ልዩ ልዩ ዓይነት ፈተና ስትፈተን ብትኖርም ሳትጠፋ ፈተናውን ሁሉ እያለፈች ከዛሬ የደረሰችው መሳሪያዋ ጠላት የማያከሽፈው፣ ዲያብሎስ የማይችለው፣ ዘመን የማይሽረው መንፈስ ቅዱስ ስለሆነ ነው፡፡

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህች ዕለት ሲናገር “ዛሬ ከበረከት ሁሉ ጫፍ ላይ ደርሰናል፤ ጌታችን የገባልንን የተስፋ ቃል ፍሬውን አግኝተናልና” ብሏል፡፡ እንዲሁም እግዚአብሔር ሊሰጥ የሚችለውን የመጨረሻውን ስጦታ በምልዓት ሰጥቶናል፤ ይህም ስጦታ ምንድን ነው ቢሉ መንፈስ ቅዱስ ነው ብሏል፡፡ በዚህም መሠረት ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይህችን ቀን “የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን” ብሏታል፡፡ (ሃይማኖተ አበው)

የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በሆነው የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ላይ ቅዱስ ሉቃስ በዚህ በዓል ዕለት የተደረገውን በተመለከተ ሲገልጽ “በዓለ ኀምሳ የተባለው ቀን በደረሰ ጊዜ ሁሉም በአንድ ልብ ሆነው አብረው ሳሉ ድንገት እንደሚነጥቅ ዐውሎ ነፋስ ከሰማይ ድምጽ መጣ፤ ተቀምጠውም የነበሩበትን ቤት ሁሉ ሞላው፤ እንደ እሳት የተከፋፈሉ ልሳኖች ታዩዋቸው በእያንዳንዳቸውም ላይ ተቀመጡባቸው፤ በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው መንፈስም ይናገሩ ዘንድ እንደሰጣቸው በሌላ ልሳኖች ይናገሩ ጀመር፡፡” በማለት ጽፏል(ሐዋ. ፪ ፥ ፩ – ፬)፡፡

መንፈስ ቅዱስ በጌታችን ጥምቀት ጊዜ በርግብ አምሳል እንደታየ አሁን ደግሞ ዓለሙን ሁሉ ሊለውጥ ቤተ ክርስቲያንም ልትተከል ባለበት ዕለት በአምሳለ እሳት ታየ፡፡ ለዚህም ነው ወንጌላዊው በቁሙ ነፋስ ሳይሆን እንደ ዐውሎ ነፋስ በማለት ረቂቅ አመጣጡን የገለጸው፡፡

ድንገትም እንደሚነጥቅ ዐውሎ ነፋስ ከሰማይ ድምጽ መጣ ያለውም መንፈስ ቅዱስን ነው፡፡ ይህም ስለ ምን ነው ቢሉ ነፋስ ረቅቅ ነው፣ መንፈስ ቅዱስም ረቂቅ ነውና ፤ ነፋስ ኃያል ነው መንፈስ ቅዱስም ኃያል ነውና፤ ነፋስ ፍሬውን ከገለባው ይለያል መንፈስ ቅዱስም ጻድቃንን ከኃጥአን ይለያልና፤ ነፋስ በምልዓት ሳለ አይታወቅም መንፈስ ቅዱስም በምልዓት ሳለ አይታወቅም፤ ነፋስ ባሕር ሲገስጽ ዛፍ ሲያናውጥ ነው እንጂ አይታወቅም መንፈስ ቅዱስም ቋንቋ /ልሳን/ ሲያናግር ምሥጢር ሲያስተረጉም ነው እንጂ አይታወቅም፤ ነፋስ መዓዛ ያመጣል መንፈስ ቅዱስም መዓዛ ቅድስና ያመጣልና፡፡

በእሳት አምሳል መውረዱም እንዲሁ እሳት የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ በመሆኑ ነው፡፡ ይህም   “ወውእቱ ያጠምቀክሙ በመንፈስ ወበእሳት፤ እርሱ ግን በመንፈስ እና በእሳት ያጠምቃችኋል” በሚለው ቃለ ወንጌል ይታወቃል፡፡ (ማቴ.፫፥፲፩)

በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጠባቸው ማለቱ በእነርሱ አድሮ ሳይለያቸው ቤቱ ማደሪያው አደረጋቸው ማለት ነው፡፡ ተቀመጠባቸው የሚለው ማደር፣ ከዚያው ሳይለዩ መቀጠልን እና አለ መለየትን ያሳያልና፡፡

፩. ሐዋርያት ይህንን ታላቅ ጸጋ ያገኙ ዘንድ ብቁ ያደረጋቸው ምንድን ነው?

ሀ. በእምነት እና በትዕግሥት መጠበቃቸው(ሉቃ.፳፬፥፵፱)

ለ. ትዕዛዙን መፈጸማቸው(ሐዋ. ፭፥፳፱)

ሐ. በአንድ ልብ ሆነው ስለተጉ ነው

፪. ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን በመቀበላቸው ምን አገኙ?

ሀ. ኃይልን፣ብርታትን፣ቆራጥነትን እና ጽናትን አገኙ፡- መንፈስ ቅዱስ ኃይል ባይሰጣቸው ኖሮ መከራውን ሁሉ ተሸክመው ይጸኑ ዘንድ አይችሉም ነበር፡፡ ለዚህም ነው በጸሎተ ሐሙስ ማታ ጌታችን በፍጹም ፈቃዱ በአይሁድ እጅ በተያዘ ጊዜ ከዮሐንስ እና ከጴጥሮስ በቀር ሁሉም ፈርተው የተበታተኑት፡፡ አልክድህም ከአንተ ጋር እሞታለሁ ሲል የነበረው ጴጥሮስም በአንድ ምሽት ውስጥ ሦስት ጊዜ ነው የካደው፡፡ ተስፋ አድርጎ የተናገረውን ከመፈጸም ወደ ኋላ የማይል እግዚአብሔር በተስፋው መሠረት መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ጽናትን እና የማይዝል ብርታትን አግኝተዋል፡፡

ለ. ዕውቀትንና ማስተዋልን አገኙ፡- በዚህ ዕለት ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ከመቀበላቸው በፊት አእምሮአቸው ብዙ ምሥጢር ለመስማት እና ለመሸከም የማይችል እንደ ሕፃን አእምሮ ነበር፡፡ ጌታችን እንዲህ ሲል እንደ ተናገራቸው “የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም፤ ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፡፡”(ዮሐ. ፲፮፥፲፪-፲፫) በተስፋ ቃሉ መሠረት መንፈስ ቅዱስን ሲልክላቸው ከእነርሱ ጋር በአካል ሳለ ያስተማራቸው እና የነገራቸው ሁሉ ግልጽ ሆነላቸው አዕምሮአቸውም የእግዚአብሔርን ድንቅ እና ረቂቅ ምሥጢር የሚረዳ እና የሚያስታውል ሆነ፡፡

ሐ. በአስተሳሰባቸው ከምድራዊነት ወደ ሰማያዊነት ተሸጋገሩ፡- ዓላማቸው ሁሉ የክርስቶስን ክብር መንገር ሰዎችን ወደ እግዚአብሔር ማቅረብ ሆነ፡፡ በዚህ ዓለም የሚያስጨንቃቸው እንዴት ሀብት ንብረት እንደሚያገኙ እና እንደሚሾሙ ሳይሆን የቤተ ክርስቲያን ነገር ብቻ ሆነ፡፡ (፪ኛ ቆሮ. ፲፩-፳፰)

እንግዲህ የሐዋርያት መባረክ እና ጸጋን ማግኘት ይህን ከመሰለ እኛም በጥምቀት የምንቀበለው ጸጋ እነርሱ የተቀበሉትን መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ስለዚህ የተቀበልነውን ጸጋ መንፈስ ቅዱስ በመጀመሪያ የእርሱ ማደሪያ የሆነውን ሰውነታችንን በኃጢአት እንዳናቆሽሽ እና እንዳናሳዝነው መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡ “ለቤዛ ቀን የታተማችኁበትን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ አታሳዝኑ” (ኤፌ. ፬፥፴) እንደተባልን ሰው ከመሆን የተነሣ ውድቀቶች ቢገጥሙንም በንስሓ እናስወግዳቸው፡፡ ሐዋርያትን ያጸና አምላክ እኛንም እንዲያጸናን ክብሩን ለመውረስ እንዲያበቃን የአምላካችን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን አሜን፡፡

በእንተ ዕርገት

መምህር በትረማርያም አበባው

ዕርገት ዐርገ ዐረገ፣ ወጣ ከሚለው የግዕዝ ቃል የወጣ ቃል ሲሆን ትርጉሙ ወደ ላይ መውጣት ማለት ነው፡፡ “ነበልባሉም ከመሠዊያው ላይ ወደ ሰማይ በወጣ ጊዜ የእግዚአብሔርም መልአክ በመሠዊያው ነበልባል ውስጥ ዐረገ” (መሳ.፲፫፥፳) ከዚህ እንደምናየው ዐረገ ማለት ወደ ላይ ወጣ ማለት ነው፡፡ ይህ ቃላዊ ትርጓሜው ሲሆን ምሥጢራዊው ትርጓሜ ግን ዕርገት ማለት የሰው አምላክ መሆን ተብሎ ይተረጎማል፡፡ በዚህ አንጻር ርደት ማለት ደግሞ የአምላክ ሰው መሆን ተብሎ ይተረጎማል፡፡ “ጌታ ኢየሱስም ከእነርሱ ጋር ከተናገረ በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ በእግዚአብሔርም ቀኝ ተቀመጠ” ይላል (ማር.፲፮፥፲፱)፡፡ በዚህ አነጋገር ደግሞ የቤዛነት ሥራውን ማጠናቀቁን ያሳየናል፡፡

የዕርገት ዓይነቶች

ስለ እግዚአብሔር በምንነጋገርበት ጊዜ ግን ዐረገ ማለት ወደ ላይ መውጣትን አያመለክትም፡፡ በተመሳሳይ ወረደ ማለትም ወደ ታች መውረዱን አያመለክትም፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በሁሉ ቦታ ያለ ስለሆነ ነው፡፡ ከሰማየ ሰማያት ወረደ ብለን ስለ እግዚአብሔር ስንናገር ሰው ሆነ ወይም ተዋሐደ ብለን እንተረጉመዋለን፡፡ “አምላክ በእልልታ፣ እግዚአብሔር በመለከት ዐረገ” (መዝ.፵፯፥፭) እንዲል፡፡

ዕርገተ ክርስቶስ በሁለት ይከፈላል፡፡ እነዚህም የርኅቀት ዕርገት እና የርቀት ዕርገት ናቸው፡፡

የርኅቀት ዕርገት

በሉቃስ ወንጌል ትርጓሜ ላይ “ወእምዝ አውፅኦሙ አፍኣ እስከ ቢታንያ ወአንሥአ እደዊሁ ወአንበረ ላዕሌሆሙ ወባረኮሙ ወእንዘ ይባርኮሙ ተረኀቆሙ ወዐርገ ሰማየ፤ እስከ ቢታንያ አወጣቸው ከአጻዌ ኆኅት እስከ ፓትርያርክነት ያለውን ማዕረግ በአንብሮተ ዕድ ሾማቸው ባርኳቸው እየራቃቸው ወደ ሰማይ ዐረገ የርቀት ያይደለ የርኅቀት” ይላል (ሉቃ.፳፬፥፶)፡፡ ርኅቀት ማለት መራቅ ማለት ነው፡፡ ክርስቶስ ከትንሣኤ በኋላ በአርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡  “ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው፤ እርሱም ሲሄድ ወደ ሰማይ ትኩር ብለው ሲመለከቱ ሳሉ እነሆ…” (ሐዋ. ፩፥፱-፲) እያለ ከእነርሱ እየራቀ እየራቀ ሄዶ ተሰወራቸው፤ ለዚያም ነው ይህንን ዕርገት ኢትየጵያውያን ሊቃውንት የርኅቀት ዕርገት ብለው የሚጠሩት፡፡

የርቀት ዕርገት

ይህንን ዕርገት በተመለከተ በሃይማኖተ አበው ትርጓሜ (ሃይ. አበ.፲፯፥፱) ላይ “ወተንሥአ እሙታን አመ ሣልስት ዕለት፤ በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ በከመ ጽሑፍ በከበሩ መጻሕፍት እንደተጻፈ እንደ ተነገረ ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፤ በቅዳሴ መላእክት በክብር በብርሃን በሥልጣን ዐረገ” ካለ በኋላ የሥጋ ዕርገት በማሕፀን የቃል ዕርገት በአርባ ቀን ይላል፡፡ የቃል ዕርገት በ፵ ቀን ያለው ከላይ ያየነው የርኅቀት ዕርገትን ሲሆን ከትንሣኤ በኋላ በአርባ ቀን ማረጉን የሚያሳውቅ ነው፡፡ የሥጋ ዕርገት በማሕፀን ያለው ቃል ሥጋ ሲሆን የቃል ገንዘብ ማለትም ረቂቅነት፣ ምሉእነት፣ ሁሉን ቻይነት እና የመሳሰሉት የሥጋ ገንዘብ መሆናቸውን እና የሥጋ ገንዘብ የሆኑት ደግሞ የቃል ገንዘብ መሆናቸውን የሚያመለክት ቃል ነው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የቃል ርደት የሥጋ ዕርገት ምክንያት ናት የምንለውም ይህንን በማኅፀን የተደረገውን ረቂቅ ዕርገት ለማመልከት ነው፡፡ ሥጋ ቃልን በመዋሐዱ ግዘፉን ሳይለቅ የቃልን ረቂቅነት ገንዘቡ አድርጓልና ይህንን ምሥጢር ሊቃውንቱ የርቀት ዕርገት ይሉታል፡፡ ይኸውም ሥጋ በማሕፀን እያለ ከቃል ጋር በመዋሐዱ በኪሩቤል ጀርባ ተቀመጠ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ በአንቀጸ ብርሃን “ወሶበ ርእዩ እግዚኦሙ ዘአስተጋብአ ኵሎ ፍጥረታተ እንዘ ይነብር ውስተ ሕፅንኪ ወዘይሴሲ ለኵሉ ፍጥረት ይጠቡ ሐሊበኪ ከመ ሕፃን ኀሠሥዎ ውስተ አርያም ወበህየ ረከብዎ ምስለ አቡሁ ወመንፈስ ቅዱስ ከመ ትካት” የሚለው ይህንን ነው፡፡ ቃልም በኪሩቤል ጀርባ ሳለ ምልአቱን ሳይለቅ በድንግል ማሕፀን ተወሰነ፡፡ መጋቢት ፳፱ ቀን ጌታ ሲፀነስ የቃል  ገንዘብ ለሥጋ፤ የሥጋ ገንዘብ የቃል የሆነበትን ቀን ቀድሞ ፍጡር የነበረ ሥጋ ፈጣሪ ሆኗልና ዐረገ ይባላል፡፡ የሥጋ ዕርገት በማሕፀን የተባለውም ሥጋ አምላክ መሆኑን ለማመልከት ነው፡፡ የቃል ዕርገት በ፵ ቀን መባሉም ቃል ሥጋን ገንዘብ በማድረጉ ከሐዋርያት ሳይለይ በሥጋ ወደ ሰማይ በማረጉ ነው፡፡

ለምን በ፵ ቀን ዐረገ?

በ፵ ቀን ማረጉ በአራተኛው ክፍለ ዘመን ሰው እንደሆነ ለማጠየቅ ነው፡፡ አራተኛው ክፍል ዘመን የተባለውም ዘመነ ካህናት ነው፡፡ የመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ዘመነ አበው፣ ሁለተኛው ክፍለ ዘመን ዘመነ መሳፍንት፣ ሦስተኛው ክፍለ ዘመን ዘመነ ነገሥት ሲሆን አራተኛው ክፍለ ዘመን ደግሞ ክርስቶስ ሰው የሆነበት ዘመነ ካህናት ነው፡፡ ሌላው አዳም በተፈጠረ በ፵ ቀን ገነት ገብቷልና የዚያ ምሳሌ፡፡ ማረጉም ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ትንቢቱም “ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ ወእግዚእነ በቃለ ቀርን” የሚለው ነው፡፡ (መዝ.፵፯፣፭) ምሳሌውም በመቅድመ ወንጌል እንደተገለጠው “ወዐርገ ውስተ ሰማያት ከመ ያለቡ ዕርገተ ጻድቃን ንጹሓን እምድኅረ ትንሣኤ ኀበ መንግሥት ዘድልው ሎሙ፤ ከትንሣኤ በኋላ በጣዕም በሥን በመዓዛ በብርሃን በክብር ተዘጋጅቶላቸው ወደ አለ ወደ መንግሥተ ሰማያት ጻድቃን መግባታቸውን ያስረዳ ዘንድ ወደ ሰማይ ዐረገ” ይላል፡፡ ጻድቃን ሁሉ በመንግሥተ ሰማያት ጸጋ እየተጨመረላቸው ለዘለዓለም የሚኖሩ መሆኑን ያስረዳል፡፡ መጽሐፈ መነኮሳት ወይትዌሰክ ሥን በዲበ ሥን እንዲል በክብር ላይ ክብር እየተጨመራቸው በማያቋርጥ ጸጋ እንደሚኖሩ የሚያስረግጥ ነው፡፡ ክርስቶስ ከትንሣኤ በኋላ በአርባኛው ቀን ወደ ሰማይ እንዳረገ ሁሉ ጻድቃንም በዳግም ምጽአት ጊዜ ከሞት ተነሥተው ወደ መንግሥተ ሰማያት ገብተው ለዘለዓለም እንደሚኖሩ ያስረዳል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

 

ዳግም ትንሣኤ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከትንሣኤ በኋላ የሚውለውን እሑድ ዳግም ትንሣኤ ብላ ሰይማ ታከብረዋለች፡፡ ይህም በአከባበር፥ በሥርዓት የመጀመሪያውን ትንሣኤ ስለሚመስል ነው፡፡ ከትንሣኤ ዋዜማ ጀምሮ የሚጸለየው ጸሎት፣ የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር ሳይለወጥ፤ በሙሉ በዚህ ቀንም ይደገማል፡፡

ዕለቱንም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ለሁለተኛ ጊዜ መታየቱን(መገለጡን) በማሰብ ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡ የሐዋርያው ቅዱስ ቶማስም ምስክርነት የሚታሰብበት ነው፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡-

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዐርብ ተሰቅሎ፣ በሦስተኛውም ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል በዝግ መቃብር ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣና በትንሣኤው ትንሣኤአችንን ካወጀልን በኋላ ሐዋርያት በአንድነት ተሰብስበው ሳለ ተገልጦላቸዋል፡፡ ይህንንም ወንጌላውያኑ በመተባበር ገልጸውታል፡፡ በተለይ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ “ያም ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን በመሸ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ አይሁድን ስለ ፈሩ ተሰብስበው የነበሩበት ቤት ደጁ ተቆልፎ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ በመካከላቸው ቆመና ‘ሰላም ለእናንተ ይሁን’ አላቸው፡፡ ይህንም ብሎ እጆቹንና ጎኑን አሳያቸው፤ ደቀ መዛሙርቱም ጌታችንን ባዩት ጊዜ ደስ አላቸው”(ዮሐ.፳፥፲፱-፳፤ማቴ.፳፰፥፲፮-፳፤ሉቃ.፳፬፥፴፮-፵፱) በማለት ገልጾታል፡፡

ይህ ሁሉ ሲሆን ግን ዲዲሞስ የተባለው ቶማስ አብሯቸው አልነበረምና የሆነውን ቢነግሩት አላምንም አለ፡፡ ይህንንም ወንጌላውያኑ ሲገልጹት “… ጌታችንን አየነው” አሉት፡፡ እርሱ ግን “የችንካሩን ምልክት በእጁ ካላየሁ፤ ጣቱንም ወደተቸነከረበት ካልጨመርሁ፤ እጄንም ወደ ጎኑ ካላስገባሁ አላምንም” አላቸው፡፡ (ዮሐ.፳፥፳፬-፳፭)፡፡

ከስምንት ቀን በኋላም ሐዋርያት፣ ካላየሁ አላምን ያለው ቶማስን ጨምሮ በአንድነት ተሰብስበው ባሉበት በሩ እንደተዘጋ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ በመካከላቸውም ቆመ፡፡ እንዲህም አላቸው፡- “ሰላም ለእናንተ ይሁን”፡፡ ከዚህም በኋላ ቶማስን “ጣትህን ወዲህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና ወደ ጎኔ አግባ፤ እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን” አለው፡፡ ቶማስም ”ጌታዬ አምላኬም” ብሎ መለሰ፡፡ ጌታችን ኢየሱስም “ስለአየኸኝ አመንህን? ብፁዓንስ ሳያዩ የሚያምኑ ናቸው” አለው፡፡ (ዮሐ.፳፥፳፮-፳፱)፡፡

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን ዕለት ዳግም ትንሣኤ ብላ ሰይማ ሥርዓቱንም እንደ ትንሣኤው ትፈጽማለች፣ በድምቀት ታከብራለች፡፡

በዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፡-

  • በገባሬ ሰናይ ዲያቆን፡- (፩ቆሮ.፲፭፥፩-፳)
  • በንፍቅ ዲያቆን፡- (፩ዮሐ.፩፥፩- ፍጻሜው)
  • በንፍቅ ቄስ፡- (ሐዋ.፳፫፥፩-፲)
  • ወንጌል፡- (ዮሐ.፳፲፱-ፍጻሜው)
  • ቅዳሴ፡- የዲዮስቆሮስ

የክርስቶስ ትንሣኤ በሊቃውንት

የጌታችን መድኀኒታችን ኤሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በተመለከተ በተለያዩ ዘመናት የተነሡ አባቶቻችን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ብዙ አስተምረዋል፣ ጽፈዋል፡፡ ለዛሬ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መጻሕፍት መካከል በሃይማኖተ አበው ያገኘውን በጥቂቱ እናቀርባለን፡፡

“ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ ‘በትንሣኤ ከእናንተ ጋር እስከምመጣበት ቀን ድረስ ከዚያ ወይን ጭማቂ አልጠጣም፤ በሐዲስ ግብር በምነሣበት ጊዜ የምታዩኝ እናንት ምስክሮቼ ናችሁ’ ያለውን የማቴዎስን ወንጌል በተረጐመበት አንቀጽ እንዲህ አለ፤ ሐዲስ ያለው ይህ ነገር ምንድን ነው? ይህ ነገር ድንቅ ነው! መዋቲ ሥጋ እንዳለኝ ታያላችሁ፤ ነገር ግን ከትንሣኤ በኋላ የማይሞት ነው፤ አይለወጥም፤ ሥጋዊ መብልንም መሻት የለበትም፤ ከትንሣኤ በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ቢበላም ቢጠጣም መብልን ሽቶ አይደለም፤ እርሱ ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሣ ያምኑ ዘንድ በላ ጠጣ እንጂ፡፡ ይህ ድንቅ ሥራ ነው! ያለ መለወጥ ሰው የኾነ ቃል የተቸነከረበትን ምልክት (እትራት) አላጠፋምና፡፡ በሚሞቱ ሰዎች እጅ እንዲዳሠሥ አድርጎታልና፡፡ አምላክ የኾነ ሥጋ የሚታይበት ጊዜ ነውና አላስፈራም፡፡ እርሱ በዝግ ደጅ ገባ፤ ግዙፉ ረቂቅ እንደ ኾነ ሥራውን አስረዳ፡፡ ነገር ግን በትንሣኤው ያምኑ ዘንድ የተሰቀለው እርሱ እንደሆነ የተነሣውም ሌላ እንዳይደለ ያውቁ ዘንድ ይህን ሠራ፡፡ ስለዚህም ተነሣ፤ በሥጋውም የችንካሩን ምልክት (እትራት) አላጠፋም፤ ዳግመኛም ከትንሣኤው አስቀድሞ ደቀ መዛሙርቱ ጧት ማታ ከእርሱ ጋር ይበሉ እንደ ነበረ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በላ፤ ስለዚህም በአራቱ መዓዝነ ዓለም ትንሣኤውን አስረዱ፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ‘ያየነው ከእርሱም ጋር የበላን የጠጣንም እርሱ ነው’ ብለው አስረዱ” (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሃይ. አበ. ፷፮፥፯-፲፪)፡፡

“ክርስቶስ የሙታን በኵር እንደምን ተባለ? እነሆ በናይን ያለች የድሀይቱን ልጅ አስቀድሞ አስነሣው፤ ዳግመኛም አልዓዛርን በሞተ በአራተኛው ቀን አስነሣው፡፡ ኤልያስም አንድ ምውት አስነሣ፡፡ ደቀ መዝሙሩ ኤልሣዕም ሁለት ሙታንን አስነሣ፤ አንዱን ሳይቀበር፣ ሁለተኛውን ከተቀበረ በኋላ ሥጋውን አስነሣ፡፡ እነዚያ ሙታን ቢነሡ ኋላ እንደ ሞቱ፤ እነርሱ ኋላ አንድ ኾነው የሚነሡበትን ትንሣኤ ዛሬ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሙታን ትንሣኤያቸው በኵር ነው፡፡ ‘እንግዲህ ወዲህም ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ የተነሣ እርሱ ነው፤ ዳግመኛም ሞት አያገኘውም’ ተብሎ እንደ ተጻፈ” (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፯፥፫-፮)፡፡

“ከሙታን ተለይቶ ተነሥቶ ሲኦልን ረግጦ፣ በሞቱ ሞትን አጠፋው፤ በሦስተኛው ቀንም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ‘አባት ሆይ፤ አመሰግንሃለሁ’ ብሎ ሥግው ቃል አመሰገነ” (እልመስጦአግያ ዘሐዋርያት ፭፥፩)፡፡

“የሥጋን ሕማም ለመለኮት ገንዘብ በአደረገ ጊዜ የእግዚአብሔር አካል በባሕርዩ በግድ ሕማምን አልተቀበለም፤ ሕማም በሚስማማው ባሕርዩ ኃይልን እንጂ፡፡ ሞትም በሥጋ ለእግዚአብሔር ቃል ገንዘብ በኾነ ጊዜ ሞትን አጠፋ፡፡ ከሞትም በኋላ ፈርሶ፣ በስብሶ መቅረትን አጠፋ” (ቅዱስ ቴዎዶጦስ ሃይ. አበ. ፶፫፥፳፯)፡፡

“እንደ ሞተ እንዲሁ ተነሣ፤ ሙታንንም አስነሣ፡፡ እንደ ተነሣም እንዲሁ ሕያው ነው፤ አዳኝ ነው፡፡ በዚህ ዓለም እንደ ዘበቱበት፣ እንደ ሰደቡት፣ እንዲሁ በሰማይ ያሉ ዅሉ ያከብሩታል፤ ያመሰግኑታል፡፡ ለሥጋ በሚስማማ ሕማም ተሰቀለ፤ በእግዚአብሔርነቱ ኃይል ተነሣ፤ ይኸውም መለኮቱ ነው፡፡ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ማረከ” (ቅዱስ ሄሬኔዎስ፣ ሃይ. አበ. ፯፥፳፰-፴፩)፡፡

“እንዲህ ሰው ኾኖም ሰውን ፈጽሞ ያድን ዘንድ ታመመ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ” (ሠለስቱ ምዕት፣ ሃይ. አበ. ፲፱፥፳፬)፡፡

“ሞትን ያጠፋው፣ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ የሞት ሥልጣን የነበረው ዲያብሎስን የሻረው እርሱ ነው፡፡ ሰው የኾነ፣ በሰው ባሕርይ የተገለጠ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔር ያደረበት ዕሩቅ ብእሲ አይደለም፤ ሰው የኾነ አምላክ ነው እንጂ፡፡ ፈጽሞ ለዘለዓለሙ በእውነት ምስጋና ይገባዋል” (ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ሃይ. አበ. ፳፭፥፵)፡፡

ይቆየን፡፡

ቀዳም ሥዑር

በሰሙነ ሕማማት በስቀለት ማግስት የሚውለው ቅዳሜ ቀዳም ሥዑር በመባል ይጠራል፡፡ በዚህ ዕለት ከድሮው በተለየ መልኩ ጌታችን መድኂታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ አገዛዝና እስራት ነጻ ለማውጣት የተቀበለውን መከራ፣ እንዲሁም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ማደሩን በማሰብ በጾም ታስቦ ስለሚውል ቀዳም ስዑር ወይም የተሻረው ቅዳሜ ተብሏል፡፡ የማይጾመው ቅዳሜ ስለሚጾም ስዑር /የተሻረ/ ተብሏል፡፡

ቀዳም ሰዑር ሌሎችም ስያሜዎች ያሉት ሲሆን እንደሚከተለው ቀርቧል፡-

ለምለም ቅዳሜ፡-

ካህናቱ ሌሊት ለምእመናን ለምለም ቄጤማ ስለሚያድሉ ዕለቲቱ በዚህ ስያሜ ተሰይሟል፡፡ ቀጤማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤ ሌሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል፡፡

በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለ ዓዋዲ/ እየመቱ “ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ” የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር፤ ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ቄጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሠሩበትን ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡

የቀጤማው አመጣጥና ምስጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ /በጥፋት ውኃ/ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሰረችው ቄጤማ ይዛ በመግባት ነው፡፡

ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጢአት ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ ታወጀ በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበሥሩበታል፡፡

ቅዱስ ቅዳሜ

ቅዱስ ቅዳሜ መባሉ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን ከሥራው ሁሉ ያረፈበት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ሥራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ፣ በነፍሱ ሲዖልን በርብሮ ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየ ዕለት ለማለት ቅዱስ ቅዳሜ ተብሏል፡፡

ሰባቱ የመስቀል ላይ ጩኸቶች

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአይሁድ በይሁዳ አማካይነት ተላልፎ ከተሰጠበት ሐሙስ ምሽት ጀምሮ ስቃይ ሲያጸኑበት ቆይተዋል፡፡ በዕለተ ዐርብም ይሰቅሉት ዘንድ አስከ ቀራንዮ መስቀል አሸክመው የተለያዩ ጸዋትወ መከራ እያጸኑበት ወስደውታል፡፡ በመሰቀል ላይ በሁለቱ ወንበዴዎች መካከል ከተሰቀለበት ሰዓት ጀምሮም የተናገራቸው ቃላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን “ሰባቱ የመስቀል ላይ ጩኸቶች ወይም “ሰባቱ አጽርሐ መስቀል” በማለት ሰይማ ታስባቸዋለች፡፡ እነርሱም በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱ ሲሆን ቀጥለንም በዝርዝር እንመለከታቸዋለን፡-

፩ኛ. “ኤሎሄ ኤሎሄ ላማሰበቅታኒ፤ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ”፡-

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሳለ በዘጠኝ ሰዓት የተናገረው ቃል እንደሆነ በወንጌል ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ “በዘጠኝ ሰዓትም ጌታችን ኢየሱስ ኤሎሄ ኤሌሄ ላማሰበቅታኒ ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸ፡፡ይኸውም አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ? ማለት ነው፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት በሰሙ ጊዜ ይህስ ኤልያስን ይጠራል አሉ” (ማቴ.፳፯፥፵፭) እንዲል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ ብሎ የተናገረበት መሠረታዊ ሐሳብ፡- ያችን የድኅነት ቀን ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ያለችውን ዕለተ ዓርብ በተስፋ ይጠባበቅ የነበረውን አዳምን ወክሎ እንደሆነ አበው ያስረዳሉ፡፡ (ማቴ.፳፯፥፵፭ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡ በመሆኑም አምላኬ አምላኬ ያለው በአዳም ተገብቶ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እንዲሁም አምላኬ አምላኬ ያለው ሰውነቱን ሲገልጥ ነው፡፡ ይህም ፍጹም አምላክነቱንና ፍጹም ሰውነቱን ማለት ነው፡፡

፪ኛ. “ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ”፡-

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደል ሳይኖርበት እንደ በደለኛ ተቆጥሮ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ነበር የተሰቀለው፡፡ “ከእርሱ ጋርም ሁለት ወንበዴዎችን አንዱን በቀኙ አንዱን በግራው ሰቀሉ፡፡ መጽሐፍ ከዐመፀኞች ጋር ተቈጠረ ያለው ተፈጸመ” (ማር.፲፭፥፳፯) ይላልና፡፡

በቀኝ በኩል የተሰቀለው ወንበዴ ጌታችንን “አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ›” አለው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ እንዲህ አለው “እውነት እልሃለሁ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ፡፡” (ሉቃ.፳፫፥፵፫)፡፡

፫ኛ. “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ”፡-

“ያን ጊዜም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድምጹን ከፍ አድርጎ አባት ሆይ ነፍሴን በአንተ እጅ አደራ እሰጣለሁ ብሎ ጮኸ፤ ይህንም ብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ሉቃ.፳፫፥፵፮)፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” በማለት የተናገረው ቃል የተሰቀለው እርሱ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነና የአብ የባሕርይ ልጁ እንደሆነ ያሳያል፡፡

፬ኛ. “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው”፡-

ምንም በደል ሳይኖርበት አይሁድ በክፋት ተነሳስተው መከራ አጸኑበት፤ ያን ሁሉ የግፍ ግፍ በጭካኔ የተሞላ መከራ ሲያደርሱበት ልባቸውን ዲያብሎስ ስላደነዘዘው የሚራራ ልብ አጡ፡፡በዚያንም ጊዜ መምህረ ይቅርታ ቸሩ አምላካችን ለሠቃዮቹ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው አለ” (ሉቃ.፳፫፥፴፬)፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደለኞች ይቅርታን ያገኙ ዘንድ ይቅር በላቸው አለ፡፡ ልመናውንም ያቀረበው ወደ ባሕርይ አባቱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ጋር ደግሞ በባሕርይ፣ በሕልውና፣ በአገዛዝ፣ በፈቃድ አንድ ናቸው፡፡ እንዲሁም የሰውን ባሕርይ ባሕርይ አድርጎ ፍጹም ሰው እንደሆነ ሲያስረዳ ነው፡፡ይህም በደለኞችን ከራሱ ጋር ያስታረቀበት የፍቅር ድምጽ ነው፡፡

አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅርበላቸው ማለቱ አባት ሆይ ብሎ የባሕርይ ልጅነቱን ከመግለጹ በተጨማሪ ይቅር በላቸው ማለቱ ጠላትን ይቅር ማለት የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ የመሆኑ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ምክንያቱም ጠላቶቻችሁን ውደዱ ብሎ ያስተማረ እርሱ ብቻ ነውና፡፡

፭ኛ. “እነሆ ልጅሽ፤ እናትህ እነኋት”፡-

“ጌታችን መድኀኒታችንን ኢየሱስም እናቱንና የሚወደውን ደቀ መዝሙሩን ቆመው ባያቸው ጊዜ እናቱን ‘አንቺ ሆይ እነሆ ልጅሽ’ አላት፡፡ ከዚህም በኋላ ደቀ መዝሙሩን ‘እናትህ እነኋት’ አለው፡፡ ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ተቀብሎ ወደ ቤቱ ወሰዳት” (ዮሐ.፲፱፥፳፮)፡፡ ደቀ መዝሙሩ ተብሎ የተጠቀሰው ጌታችን ይወደው የነበረ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊው ነው፡፡ ይህንንም የጻፈው እርሱ ነው (ዮሐ.፳፩፥፳፬)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ከዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት አንዱ ቢሆንም ሐሙስ ማታ እረኛው ሲያዝ ከተበተኑት በጎች ጋር አብሮ አልሸሸም፡፡ በዚያች በአስጨናቂዋ ሰዓት ከጌታችን ጋር እስከ እግረ መስቀሉ ተጓዘ፡፡የክርስቶስ ፍቅር ፍርሃቱን ሁሉ አርቆለት የአይሁድን ቁጣና ዛቻ ሳይፈራ ጸንቶ በመቆሙ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለእኛ ሁሉ እርሱ በኩል ተሰጠችን፡፡ እናታችን ድንግል ቅድስት ማርያም ሁል ጊዜም ቢሆን ከእግረ መስቀሉ ሥር ለሚገኙ፣ ልባቸው ቀራንዮን ለሚያስብ ሁሉ እናት እንድትሆን እነርሱም ልጆቿ እንዲሆኑ በቅዱስ ዮሐንስ በኩል ተሰጥታናለች፡፡

በመሆኑም “እነሆ ልጅሽ፤ እናትህ እነኋት” የሚለው የመስቀሉ ቃል በመስቀል ላይ የተከፈለልንን ዋጋ አስበን በእርሱ አምነን በምግባር ታንጸን እንደ ፈቃዱ በምንኖር ክርስቲያኖችና ለድኅነታችን ምክንያት በሆነች በእመ አምላክ በቅድስት ድንግል ማርያም መካከል የእርሷ እናትነት፣ የእኛ ልጅነት የተመሠረተበት የፍቅር ቃል ነው፡፡

፮ኛ. “ተጠማሁ”፡-

“ከዚህም በኋላ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ሁሉ እንደ ተፈጸመ ባየ ጊዜ የመጽሐፍ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‘ተጠማሁ’ አለ” (ዮሐ.፲፱፥፳፰)፡፡

ውኆችን በእፍኙ የሰፈረ፣ የባሕር አሸዋን የቆጠረ፣ ውኆችንም ጠርቶ በምድር ፊት ላይ የሚያፈሳቸው፣ የባሕር ጥልቀትንና ዳርቻን የወሰነ፣ የኤርትራን ባሕር እንደ ግድግዳ ያቆመ አምላክ “ተጠማሁ” ብሎጮኸ፡፡ (ኢሳ.፵፥፲፪፣አሞ.፱፥፮)፡፡

“የተጠማ ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ በእኔም የሚያምን መጽሐፍ እንደ ተናገረ የሕይወት ውኃ ምንጭ ከሆዱ ይፈልቃል” (ዮሐ.፯፥፴፯) በማለት እርሱ የሕይወት ውኃ እንደሆነ ተናገረ፡፡ አምላክ ሲሆን “ተጠማሁ” ብሎ መጮኹ ስለ ምንድንነው ብለን ቅዱሳት መጻሕፍትን ስንመረምር፡- አንደኛ የመከራውን ጽናት፣ ከሚነገረው በላይ መከራውን እንዳጸኑበት የሚያሳይ ሲሆን፤ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ እርሱ የተጠማው የሰውን መዳን ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በዚያን ወቅት እንኳ ከክፉ ሥራው ተመልሶ የሚጸጸት፣ የሚራራ፣ ንስሓ የሚገባ ሰው በማጣቱ መድኃኒት እርሱ ቀርቦ ሳለ የሰው ልጅ ባለማስተዋሉ ወደ እርሱም በፍቅር ባለመቅረቡና ባለመመለሱ ተጠማሁ አለ፡፡

፯ኛ. “ሁሉ ተፈጸመ”፡-

”ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስም ሆምጣጤውን ቀምሶ ሁሉ ተፈጸመ አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ዮሐ.፲፱፥፴)፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕተ ዐርብ በመስቀል ላይ ሳለ ‘ተፈጸመ’ ብሎ መናገሩ ብዙ ትርጉም ያለው ቃል ነው፡፡ እነርሱም፡-

 በነቢያት ስለ እኔ የተነገረው ትንቢት፣ የተመሰለው ምሳሌ፣ በቅዱሳን አበው የተቆጠረው ሱባኤ፣ ጊዜው ደርሶ የአዳም ተስፋ ተፈጸመ፡፡

 የሰው ልጅ በዲያብሎስ አገዛዝ በሞትና በጨለማው ሥልጣን፣ በአጋንንት ወጥመድ ታስሮ የሚኖርበት የፍዳ ዘመን አለቀ ተፈጸመ፡፡

 በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰማይና በምድር መካከል ቆሞ የነበረው የጥል ግድግዳ ፈረሰ፣ የተጻፈው የዕዳ ጽሕፈት ተደመሰሰ፣ የሰው ልጅ ዕዳ በደል ተከፈለ በአምላክ የቤዛነት ሥራ ሁሉ ተፈጸመ ማለት ነው፡፡

እነዚህ ከአንድ እስከ ሰባት የጠቀስናቸው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መራራውን መከራ እየተቀበለ የተናገራቸው የመጨረሻ ቃላቶቹ ናቸው፡፡ ወደዚህ ዓለም ሰው ሆኖ የመጣበትን ዓላማ አከናውኖ ሲጨርስ በመጨረሻ “ተፈጸመ ኵሉ” በማለት ነፍሱን ከሥጋው ለየ፡፡ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶም በሲኦል ባርነት ለነበሩት አዳምና ልጆቹ ነጻነትን ሰበከላቸው፡፡ በአካለ ሥጋ ደግሞ ወደ መቃብር ወርዶ ሙስና መቃብርን አጠፋልን፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን፡፡

ጸሎተ ሐሙስ

ጸሎተ ሐሙስ ጌታችን ምሥጢረ ቊርባንን ከምሥጢረ ጸሎት ጋር አዋሕዶ የገለጠበት ዕለት ነው፡፡ በወንጌልም እንደተጻፈው ፋሲካውን የሚያከብሩበት ቀን ሲደርስ ጌታ ኢየሱስም ጴጥሮስንና ዮሐንስን ሒዳችሁ ፋሲካን እንበላ ዘንድ አዘጋጁልን አላቸው፤ እነርሱም በየት እንድናዘጋጅልህ ትወዳለህ አሉት? ወደ ከተማ ገብታችሁ የውኃ ማድጋ የሚሸከም ስምዖን የተባለ ሰው ታገኛላችሁ፤ ወደ ገባበት ቤት እርሱን ተከተሉት፤ መምህር ከደቀ መዛሙርቶቼ ጋር ፋሲካ የሚያደርግበት አዳራሽ ወዴት ነው ይልሃል? በሉት እርሱ የተነጠፈውንና ታላቁን አዳራሽ ያሳያችኋል፤ በዚያም ፋሲካን አዘጋጁልን አላቸው፤ እነርሱም ወደ ተላኩበት ከተማ ገብተው አልዓዛርን የውኃ ማድጋ ተሸክሞ አገኙት፡፡ ጴጥሮስና ዮሐንስም ለስምዖን ጌታ በቤቱ ፋሲካን ሊያዘጋጅ መሻቱ እንደሆነ ነገሩት፤ እርሱም የፍጥረታት ጌታ በቤቱ ሊመጣ እንዳለ አስቦ ተደሰተ፤ ወደ ሚስቱ አክሮሲናም ሔዶ ይህ አልዓዛርን ከሞት ያስነሳ እኔንም በኃጢአቴ ይቅር ይለኛል፤ ያነጻኝ ዘንድ ከሐዋርያት ጋር በቤታችን ይመጣል አላት፤ አክሮሲናም እጅግ ተደሰተች፡፡

ጌታችንም ጊዜው ሲደርስ ከሐዋርያት ጋር በአንድነት መጣ፤ ስምዖንም ከቤቱ ወጥቶ ሮጦ ከጌታ እግር ሥር ሰገደ፤ ወደ ቤቱም ከሐዋርያት ጋር አስገባቸው፡፡ ይሁዳ ግን ይህን ሰዓት አልነበረም፤ ውጪ ከሻጭና ለዋጭ ጋር ገንዘብ ሲደራደር ነበር፤ ስምዖንም ለሚስቱ አክሮሲና ጌታና ሐዋርያት የሚገቡበት በእግራቸው የሚረግጡት ምንጣፍ እንድታነጥፍ አዘዛት፡፡ አክሮሲና ግን የጌታን መልክ አታውቀውም ነበር፤ ያን ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ጸሎት ሲጸልዩ አይታ ‹‹ከእናንተ ውስጥ መምህሩ ማነው›› አለቻቸው፤እነርሱም ዝም አሉ፤ መልከ መልካም ወደ ሆነውና የጌታ ወዳጅ ወደሆነው ዮሐንስ ተመልክታ እርሱ ይሆን አለች፤ ጴጥሮስ ግን ቀበል አድርጎ ‹‹ጌታ ኢየሱስ ከውስጠኛው ክፍል ቆሞ ይጸልያል፤ ጌታ እርሱ ነው›› አላት፡፡ እርሷም ገብታ ሰገደችለት፤ ይሁዳም በመጨረሻ ሳጥን ተሸክሞ መጣ፤ ጠባቂውንም እኔ የጌታ ደቀ መዝሙር ነኝ አለው፡፡ በር ጠባቂውም እለእስክንድሮስም የተነጠፈውን እስካጥፍ ጠብቅ ብሎ ዘለፈው፤ ልብሱንም አንስቶ አስገባው፤ /ግብረ ሕማማት ፭፻፹፫-፫፻፹፭/፡፡

ጸሎተ ሐሙስ በብሉይ ኪዳን

ጸሎተ ሐሙስ በብሉይ ኪዳን ለፋሲካ ዝግጅት ተደርጎበታል (ማቴ. ፳፮፥፯-፲፫)፡፡ ‹ፋሲካ› ማለት ማለፍ ማለት ነው፡፡ ይኸውም እስራኤላውያን በግብጽ ምድር ሳሉ መልአኩን ልኮ እያንዳንዱ እስራኤላዊ የበግ ጠቦት እንዲያርድና ደሙን በበሩ ወይም በመቃኑ እንዲቀባ ለሙሴ ነገረው፡፡ ሙሴም የታዘዘውን ለሕዝቡ ነገረ፤ ዅሉም እንደ ታዘዙት ፈጸሙ፡፡ በኋላ ከእግዚአብሔር ዘንድ መቅሠፍት ታዞ መልአኩ የደም ምልክት የሌለበትን የግብጻውያንን ቤት በሞተ በኵር ሲመታ፤ የበጉ ደም ምልክት ያለበትን የእስራኤላውያንን ቤት ምልክቱን እያየ አልፏል፡፡ ፋሲካ መባሉም ይህን ምሥጢር ለማስታወስ ነው (ዘፀ. ፲፪፥፩-፳)፡፡

በዚህ መነሻነት በየዓመቱ እስራኤላውያን በመጀመሪያው ወር በዐሥራ አራተኛው ቀን በግ እያረዱ የፋሲካን በዓል ያከብራሉ፡፡ አገራችን ኢትዮጵያም አስቀድማ ብሉይ ኪዳንን የተቀበለች አገር እንደ መኾኗ ይህን ሥርዓት ትፈጽም ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳንም የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ‹ፋሲካ› ተብሎ የተጠራበት ምክንያት ጌታችን በዚህ በፋሲካ በዓል ራሱን የተወደደ ምሥዋዕት አድርጎ ደሙን ስላፈሰሰልን ነው፡፡ በደሙ መፍሰስም ሞተ በኵር የተባለ ሞተ ነፍስ ርቆልናል፡፡ ስለዚህም ክርስቶስን ‹ፋሲካችን› እንለዋን (፩ኛ ቆሮ. ፭፥፯፤ ፩ኛ ጴጥ. ፩፥፲፰-፲፱)፡፡

የጸሎተ ሐሙስ ስያሜዎች

 ጸሎተ ሐሙስ

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አይሁድ ያደረሱበትን መከራ በማሰብ የዐቢይ ጾም ስምንተኛ ሳምንት ሆሳዕና ማግስት ጀምሮ ሰሙነ ሕማማትን በሐዘን፣ በጸሎትና በስግደት ታሳልፈዋለች፡፡ ለቀናቱንም የተለያየ ስያሜ ሰጥታ ሥርዓቱን ታከናውናለች፡፡ በዚህም መሠረት፡-

  • ሰኞ፡– አንጽሆተ ቤተ መቅደስ(በቤተ መቅደስ ሲሸጡና ሲለውጡ የነበሩትን ያስወጣበት) ፣ እንዲሁም አምላክ ሲሆን የእኛን ሥጋ ተዋሕዷልና ተራበ፡፡ ለምልማ ከነበረችው በለስ ፍሬ ይበላ ዘንድ ጎበኛት ነገር ግን ፍሬ አጣባት፡፡ በለሷንም ረገማት፡፡ ስለዚህም መርገመ በለስ ተባለ፡፡
  • ማክሰኞ:የጥያቄ ቀን፣ የትምህርት ቀን
  • ረቡዕ፡- የምክር ቀን (አይሁድ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይገድሉት ዘንድ የተማከሩበትና ውሳኔ ያሳለፉበት ቀን ነው፡፡ ይሁዳም በሰላሣ ብር አሳልፎ ሊሰጣቸው የተስማማበት ቀን ነው፡፡

 ጸሎተ ሐሙስ

ስለ ሦስቱ የሰሙነ ሕማማት ዕለታት ይህን ያህል ካልን ጽሁፋችንን ጸሎተ ሐሙስ ላይ ትኩረት አድርገን እንቀጥላለን፡-

ጸሎተ ሐሙስን ሕፅበተ ሐሙስ፣ የምስጢር ቀን፣ የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ፣ የነፃነት ሐሙስ እየተባለም ይጠራል፡፡

ሕጽበተ ሐሙስ

ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በፍጹም ትሕትና ዝቅ ብሎ አጥቧል፡፡ ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ የንጽሕና፣ የቅድስና አምላክ መሆኑን ያጠይቃል፡፡ ስለዚህም ዕለቱ “ሕጽበተ ሐሙስ” ይባላል፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ሊቃነ ጳጳሳትና ቀሳውስት በመካከላችን ተገኝተህ የእኛንና የሕዝብህን ኃጢአት እጠብ፤ እኛም የአንተን አርአያነት ተከትለን የልጆቻችንን እግር እናጥባለን” ሲሉ በቤተ ክርስቲያን የተገኙ ምእመናንን እግር በወይንና በወይራ ቅጠል ያጥባሉ፡፡

የምሥጢር ቀን

ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንዱ ምሥጢረ ቍርባን በዚህ ቀን ተመሥርቷልና ዕለቱ “የምሥጢር ቀን” ይባላል፡፡ ይኸውም ጌታችን ኅብስቱንና ጽዋውን አንሥቶ ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቈረሰው ሥጋዬ ነው፡፡ እንካችሁ፤ ብሉ፡፡ ይህ ስለ እናንተ ነገ በመስቀል ላይ የሚፈስ ደሜ ነው፤ ከእርሱም ጠጡ በማለት እርሱ ከእኛ፤ እኛም ከእርሱ ጋር አንድ የምንሆንበትን ምሥጢር ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ፣ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ስያሜ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሐ ታጥቦ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል ይዘጋጃል፡፡

የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ

መድኃኒታችን ክርስቶስ መሥዋዕተ ኦሪት ማለትም በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ፣ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ይህ ዕለት “የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ” ይባላል (ሉቃ. ፳፪፥፳)፡፡ “ኪዳን” ማለት በሁለት ወገን መካከል የሚደረግ ውል፣ ስምምነት፣ መሐላ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ጌታችን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ዘለዓለማዊውን ቃል ኪዳን በራሱ ደም የፈጸመበት ዕለት ስለ ሆነ ሐሙስ “የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ” ተባለ፡፡

የነጻነት ሐሙስ

ይህ ዕለት ለኃጢአትና ለዲያብሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱ የተገለጠበት፤ የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለ ሆነ “የነጻነት ሐሙስ” ይባላል፡፡ ጌታችን ስለ ሰው ልጅ ነጻነት ሲናገር ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፡፡ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ በማለት ከባርነት የወጣንበትን፤ ልጆች የተባልንበትን ቀን የምናስብበት በመኾኑ “የነጻነት ሐሙስ” ይባላል (ዮሐ. ፲፭፥፲፭)፡፡ እያንዳንዱ ክርስቲያንም ከኃጢአት ባርነት ርቆ፣ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያወዳጀውን መልካም ሥራ በመሥራት ሕይወቱን መምራት ይኖርበታል፡፡ ባሮች ሳይሆን ወዳጆች ተብለን በክርስቶስ ተጠርተናልና፡፡

በዚህ ዕለት እንደ ማክሰኞ ሆሉ ጌታችን በዮሐንስ ወንጌል ፲፬፥፲፮ የሚገኘውን ሰፊ ትምህርት ለደቀ መዛሙርቱ አስተምሯል፡፡ የትምህርቱም ዋና ዋና ክፍሎችም ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ያካትታሉ፡፡ ጌታችን እነዚህን ትምህርቶች በስፋትና በጥልቀት መማር እንደሚገባ ሲያስረዳ፣ ለደቀ መዛርቱ ምሥጢሩን በተአምራት ሊገልጥላቸው ሲቻለው በሰፊ ማብራርያ እንዲረዱት አድርጓል፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ያልገባቸውንም እየጠየቁ ተረድተዋል፡፡ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን መማርና ያልገባንን ጠይቀን መረዳት እንደሚገባን ከዚህ እንማራለን፡፡ መድኃኒታችን ክርስቶስ ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ የሰጠውም በዚሁ ዕለት ከምሽቱ በሦስት ሰዓት ነው (ማቴ. ፳፮፥፵፯-፶፰)፡፡

በጸሎተ ሐሙስ በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸም ሥርዓት

በዚህ ዕለት ስግደቱ፣ ጸሎቱ፣ ምንባባቱ እንደ ተለመደው ይከናወናሉ፡፡ መንበሩ (ታቦቱ) ጥቁር ልብስ ይለብሳል፡፡ ጸሎተ ዕጣን ይጸለያል፤ ቤተ ክርስቲያኑም በማዕጠንት ይታጠናል፡፡ ሕጽበተ እግር ይደረጋል፡፡ ቅዳሴ ይቀደሳል፡፡ በየቤቱ ደግሞ ጉልባን ይዘጋጃል፡፡

ሕጽበተ እግር

ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት ዲያቆኑ ሁለት ኵስኵስቶችን ውኃ ሞልቶ ያቀርባል፤ አንዱ ለእግር፣ አንዱ ለእጅ መታጠቢያ፡፡ ‹ጸሎተ አኰቴት› በመባል የሚታወቀው የጸሎት ዓይነት ይጸለያል፡፡ ወንጌል ተነቦ ውኃው በካህኑ (በሊቀ ጳጳሱ) ይባረክና የሕጽበተ እግር ሥርዓት ይከናወናል፡፡ ይኸውም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብ ያሳየውን የተግባር ትምህርት ለማሳየት ነው (ዮሐ. ፲፫፥፲፬)፡፡ ከውኃው በተጨማሪ የወይራና የወይን ቅጠልንም ለሥርዓተ ሕጽበቱ ማስፈጸሚያነት እንጠቀምባቸዋለን፡፡ ምሥጢሩም የሚከተለው ነው፡-

ወይራ ጸኑዕ ነው፡፡ ወይራ ክርስቶስም ጽኑዕ መከራ መቀበሉን ከማስረዳቱ በተጨማሪ እኛም (እግራችንን የሚያጥቡን አባቶች እና የምንታጠበው ምእመናን) መከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ሥርዓተ ሕጽበቱን በወይራ እንፈጽማለን፡፡ የወይኑ ቅጠልም መድኃኒታችን ክርስቶስ በወይን የተመሰለ ደሙን አፍስሶ ለምእመናን የሕይወት መጠጥ አድርጎ መስጠቱን ለማዘከር በወይን ሥርዓተ ሕጽበትን እናከናውናለን (ማቴ. ፳፮፥፳፮)፡፡ በቀኝና በግራ የቆሙ ሊቃውንትም ‹‹ሐዋርያቲሁ ከበበ እግረ አርዳኢሁ ሐጸበ›› እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ይህ ሥርዓት ከተጠናቀቀ በኋላ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ምእመናን ይቀበላሉ፡፡

 ቅዳሴ

የጸሎተ ሐሙስ ቅዳሴ የሚከናወነው በተመጠነ ድምፅ ሲሆን፣ እንደ ደወል (ቃጭል) የምንጠቀመውም ጸናጽልን ነው፡፡ ልኡካኑ የድምፅ ማጉያ ሳይጠቀሙ በለኆሣሥ (በቀስታ) ይቀድሳሉ፡፡ ምክንያቱም ይሁዳ በምሥጢር ጌታችንን ማስያዙን ለመጠቆም ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የዘመነ ብሉይ ጸሎት ዋጋው ምድራዊ እንደ ነበር ለማስታወስ ነው፡፡ በመቀጠል ክብር ይእቲ፣ ዕጣነ ሞገር፣ ዝማሬ የተባሉ የድጓ ክፍሎች ተዘምረው አገልግሎቱ ይጠናቀቃል፡፡ ሕዝቡም ያለ ኑዛዜና ቡራኬ ይሰናበታሉ፡፡

ጉልባን

ጉልባን ከባቄላ ክክ፣ ከስንዴ ወይንም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጅና የጸሎተ ሐሙስ ዕለት የሚበላ ንፍሮ ነው፡፡ በጸሎተ ሐሙስ በቤት ውስጥ ከሚፈጸሙ ተግባራት አንዱ ጉልባን ማዘጋጀት ነው፡፡ ጉልባን እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ሲወጡ በችኮላ መጓዛቸውን የምናስታውስበት ከእስራኤላውያን የመጣ ትውፊታዊ ሥርዓት ነው፡፡ በአገራችን ኢትዮጵያ አብዛኞቹ የትውፊት ክንዋኔዎች የብሉይ ኪዳን መነሻ ስላላቸው ይህ ሥርዓት ዛሬም በኢትዮጵያውያን ምእመናን ዘንድ ይከበራል፡፡

ጉልባን እስራኤላውያን ከባርነት በወጡ ጊዜ አቡክተው፣ ጋግረው መብላት አለመቻላቸውን ያስታውሰናል፡፡ በወቅቱ ያልቦካውን ሊጥ እየጋገሩ ቂጣ መመገብ፤ ንፍሮ ቀቅለው ስንቅ መያዝ የመንገድ ተግባራቸው ነበርና፡፡ ይህን ታሪክ ለማሰብም በሰሙነ ሕማማት በተለይም በጸሎተ ሐሙስ ቂጣና ጉልባን ይዘጋጃል፡፡ በጸሎተ ሐሙስ የሚዘጋጀው ጉልባንና ቂጣ ጨው በዛ ተደርጎ ይጨመርበታል፡፡ ይኸውም ጨው ውኃ እንደሚያስጠማ ሁሉ፣ ጌታችንም በመከራው ወቅት ውኃ መጠማቱን ለማስታወስ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

 

የሰሙነ ሕማማት ዕለታት

ሰሙነ ሕማማት እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር ስለ ተገለጠበት፣ የመሥዋዕትነት ሥራ ስለ ተሠራበት፣ የሰው ልጆች ድኅነት ስለ ተፈጸመበት፣ መድኀኔዓለም በመስቀል ተሰቅሎ ለእኛ ቤዛ መኾኑ በስፋት ስለሚነገርበት ቅዱስ ሳምንት ይባላል፡፡ በተጨማሪም የመጨረሻ ሳምንት ተብሎ ይጠራል፡፡ ይኸውም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በመዋዕለ ሥጋዌው ለፈጸማቸው የቤዛነትና የአርአያነት ተግባራት ፍጻሜ በመኾኑ ነው፡፡

በዚህ ልዩ ሳምንት ካህናትና ምእመናን በነግህ፣ በሠለስት፣ በቀትር፣ በተሰዓትና በሠርክ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጓዝ ስለ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየስስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀል የሚያዘክረውን ግብረ ሕማማት መጽሐፍ እንዲሁም ከሌሎች ከቅዱሳት መጻሕፍት በማንበብና በመጸለይ ሕማሙንና ሞቱን ይዘክራሉ፡፡ ቅዱስ ያሬድ በመጨረሻው ሳምንት በየዕለቱ በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የተፈጸመውን ነገረ መስቀል በተመለከተ ባዘጋጀው መዝሙር ያመሰግናሉ፤ አብዝተው ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡

ሰሙነ ሕማማትን ከሌሎች የዐቢይ ጾም ሳምንታት ልዩ የሚያደርገው ሥርዓት አለ፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ሥርዓትና ደንብ መሠረት በሰሙነ ሕማማት ከጸሎተ ሐሙስ በስተቀር ቅዳሴ አይቀደስም፤ ስብሐተ ነግህ አይደረስም፤ ጸሎተ ፍትሐት አይጸለይም፤ ጸሎተ አስተስርዮም አይደረግም፡፡ ጥምቀተ ክርስትናም አይፈጸምም፡፡ ከላይ የተዘረዘሩት የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶች አስቀድሞ በዕለተ ሆሣዕና ይከናወናሉ፡፡ በተጨማሪም ማንኛውም ክብረ በዓል በዚህ ሳምንት ቢውል ከትንሣኤ በኋላ ይከበራል፡፡ ይህም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የጸና ኦርቶዶክሳዊ ሥርዓት ነው፡፡

ሕማምና ሞት የማይገባው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእኛን ሕማምና ሞት ለራሱ በማድረግ በዚህ ሳምንት ለእኛ ቤዛ መኾኑ ይነገራል፡፡ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ፤ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጠረ፡፡ እርሱ ግን ግፍን አላደረገም፤ ተንኮልም በአፉ አልተገኘበትም

 ተብሎ እንደ ተጻፈ (ኢሳ. ፶፫፥፬-፲፪)፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቶስ የተቀበለው የእኛን ሕማም መኾኑን በማሰብ፤ ከማንኛውም የሥጋ ሥራ በመታቀብ ዋዛ ፈዛዛ ባለመነጋገር ሰሙነ ሕማማትን እናከብራለን፡፡ ብድራትን የማያስቀረው አምላካችን እግዚአብሔር መተላለፋችንና በደላችንን በመደምሰስ የመንግሥቱ ወራሽ አድርጎናልና፡፡

በሕማማት ሳምንት ውስጥ ከሚገኙት ዕለታት መካከል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስቱ ዕለታት (ሰኞ፣ ማክሰኞ እና ረቡዕ) ያከናወናቸው የድኅነት ሥራዎች የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሰኞ

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ኾኖ በዚህ ዓለም ሲመላለስ በሆሣዕና ማግሥት ከቢታንያ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ አንደኛ፡- ከቅጠል በስተቀር ፍሬ ያልተገኘባትን ዕፀ በለስ ረግሟል፡፡ ሁለተኛ፡- ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን አስወጥቷል (ማቴ. ፳፩፥፲፪-፲፯፤ ማር. ፲፩፥፲፯፤ ሉቃ. ፲፱፥፵፭-፵፮)፡፡

ፍሬ ያልተገኘባት ዕፀ በለስን ረግሟል፡

በቅዱስ ማቴዎስ አገላለጥ በማግሥቱ ተራበ የሚል ቃል እንመለከታለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም ይላል(ኢሳ.፵፮፥፳፭)፡፡ በቅዱስ ወንጌል በመጀመሪያ ቃል እንደ ነበር፤ ያ ቃል ቀዳማዊ እንደ ኾነ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ነበር፤ ያም ቃል እግዚአብሔር እንደ ኾነ ተጽፏል (ዮሐ. ፩፥፩-፪)፡፡ ጌታችንም በመዋዕለ ትምህርቱ ሲያስተምር፡-የእኔስ መብል የላከኝን የአባቴን ፈቃድ አደርግ ዘንድ፤ ሥራውንም እንፈጽም ዘንድ ነው” ሲል ተናግሯል (ዮሐ. ፬፥፴፬)፡፡ ታዲያ ጌታችን ለምን ተራበ?

ሰማያውያን መላእክት እንዳይራቡ አድርጎ የፈጠረ፤ እስራኤልን ገበሬ በማያርስበት፣ ዘር በሌለበት፣ ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ የመገበ፤ ድኅረ ሥጋዌ በአምስት አንጀራና በሁለት ዓሣ ከአምስት ሺሕ የሚበልጡ ሰዎችን የመገበ ጌታ ተራበ  ተብሎ ሲነገር እጅግ ይደንቃል፡፡ በርግጥ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው በመኾኑ አልተራበም አንልም፡፡ የጌታችን ረኃብ የድህነት (የማጣት) አይደለም፡፡ የክርስቶስ ረኃቡ የበለስ ፍሬ ሳይኾን የሃይማኖትና የመልካም ሥነ ምግባር ፍሬ የፈለገ መኾኑን ለማጠየቅተራበ ተባለ፡፡

በለስ ብሂል ቤተ እስራኤል እሙንቱ እንዲል፡፡ ጌታችን የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረግሟል፡፡ በአይሁድ ጉባኤ የነገሠውን ኃጢአት፤ በበለስ አንጻር መርገሙን ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በአንጻረ በለስ ረገማት ለኃጢአት፤ በበለስ አንጻር ኃጢአትን ረገማት›› ብሏል፡፡

እስራኤልም በአንድ ወገን የተጠበቀባቸውን ፍሬ ባለማፍራታቸው ተረግመዋል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ እስራኤል ከፍቅር ይልቅ ርግማን እንዳገኛቸው፤ አሕዛብ ደግሞ የቃሉን ትምህርት ሰምተው የእጁን ተአምራት አይተው ያመኑበትን የእግዚአብሔር የጸጋ ልጁ ለመኾን መብቃታቸውን ሲመሰክር እንዲህ ይላል፤ አሕዛብ አስተጋብኡ ጽጌሬዳ በኂሩቱ ወሦኩሰ

ተርፈ ኀበ አይሁድ ዘውእቱ ሕፀተ ሃይማኖት፤ አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾኹ ተረፈ፡፡ ይኸውም የሃይማኖት ጉድለት ነው” ብሎ ተርጕሞታል፡፡ እሾኽ እርግማን፤ አበባ የእግዚአብሔር ጸጋ ልጅነት ምሳሌ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! ዛሬ ጌታችን ወደ መቅደስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይኾን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል “ለንስሓ የሚገባ ፍሬ አድርጉ” ይለናልና እግዚአብሔር

ከእኛ የሚፈልገውን የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ እናፍራ (ማቴ. ፫፥፰፤ ገላ. ፭፥፳፪)፡፡የሰው ልጅ

ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ሃይማኖት ያገኝ ይኾንን?” ሕይወታችንን በአምላካዊ ሥልጣኑ የቃኘ አምላክ ለፍርድ በመጣ ጊዜ የእምነት ፍሬ አፍርተን እንዲያገኘንና ዘለዓለማዊ መንግሥቱን እንዲያወርሰን የጽድቅ ሥራ ለመሥራት እንትጋ፡፡

 የሚሸጡትንና የሚለውጡትን ከቤተ መቅደስ አስወጥቷል፡-

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ አይሁድ የጸሎት ቤት የሆነውን ቤተ መቅደሱ የገበያ አደባባይ አድርገውት አገኘ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አይሁድ ያደረጉትን የማይገባ ሥራ ያስወግድ ዘንድ ይሸጡ ይለውጡ የነበሩትን ሁሉ ከቤተ መቅደሱ አስወጣ፡፡ “በቤተ መቅደስ የሚሸጡትንና የሚገዙትን ሁሉ አባረረ፤ የገንዘብ ለዋጮችንም መደርደሪያ፣ የርግብ ሻጮችንም ወንበር ገለበጠ፡፡ ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፣ ተብሎ ተጽፎአል እናንተ ግን የሌባና የቀማኛ ዋሻ አደረጋችሁት” እንዲል(ማቴ.፳፩፥፲፪-፲፫)፡፡

 ማክሰኞ

በዚህ ዕለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ ዕለቱ የትምህርት ቀን ይባላል፡፡ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃይማኖት ትምህርት ሲማር፣ ሲጠይቅ መሰንበቱ መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡ (ማቴ. ፳፩፥፳፰፤ ፳፭፥፵፮፤ ማር. ፲፪፥፲፪፤ ፲፫፥፴፯፤ ሉቃ. ፳፥፱፤ ፳፩፥፴፰)፡፡

በዚህ ዕለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሥልጣኑም ተጠይቋል፡፡ ጠያቂዎቹ የካህናት አለቆችና የሕዝብ አለቆች ሲሆኑ፣ ጥያቄውም፡- “በማን ሥልጣን እነዚህን ታደርጋለህ?

ይህንስ ሥልጣን የሰጠህ ማነው?” የሚል ነበር፡፡ ይህ ጥያቄ ጌታችን መድድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰኞ ዕለት ሁለት ነገሮችን ማከናወኑን ተከትሎ የተነሣ ጥያቄ ነው፡፡ ይኸውም ጌታችን ሲያደርጋቸው የነበሩ ተአምራትና ድንቅ ድንቅ ሥራዎች የካህናት አለቆችን ስላስቀናቸው ጌታችንን ከሮማ መንግሥት ባለ ሥልጣናት ጋር ለማጋጨት የቀየሱት ስልት ነው፡፡

ጌታችን በቤተ መቅደስ የነበሩትን ነጋዴዎችን አባሯል፤ መደባቸውን ገለባብጧል፡፡ ነጋዴን ማባረርና መደብን ማስለቀቅ መንግሥታዊ ሥራ ነው፡፡ ጌታችን በራሴ ሥልጣን ቢላቸው ፀረ መንግሥት አቋም አለው በማለት ከሮማ መንግሥት ዘንድ ለማሳጣት ነበር ዕቅዳቸው፡፡ ጌታችን ግን የፈሪሳውያንን ጠማማ አሳብ ስለሚያውቅ የዮሐንስ ጥምቀት ከየት ነው? ከሰማይ ነው

ወይስ ከምድር?” ሲል ጠይቋቸዋል፡፡ ጌታችን ፈሪሳውያን ላቀረቡለት ጥያቄ ቀጥተኛ ምላሽ አልሰጠም፡፡ ምክንያቱም ጥያቄው ለከሳሾቹ ዓላማ መሳካት አመቺ ሁኔታን ስለሚፈጥር ጥያቄውን በጥያቄ መልሶላቸዋል፡፡ እነርሱም ከሰማይ ነው ቢሉት” ለምን አላመናችሁበትም?” እንዳይላቸው፤ከሰው ነው ቢሉት ደግሞ ሕዝቡ ዮሐንስን እንደ አባት ይፈሩት፣ እንደ መምህር ያከብሩት ነበርና ሕዝቡ እንዳይጣሏቸው ስለፈሩ ከወዴት እንደ ሆነ አናውቅም ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም አላቸው፡፡ ይህን ጥያቄ መጠየቃቸውም እርሱ የሚያደርጋቸውን ተግባራት ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተውት አልነበረም፤ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ ነበር እንጂ፡፡

ዛሬም ቢሆን መልካም ሥራን በሠራን ጊዜ ከልዩ ልዩ ወገኖች የሚመጡ ፈተናዎች ለመልካም ሥራችን እንቅፋት ሊሆኑ እንደሚችሉ መገንዘብ አለብን፡፡ ብዙ ወገኖች ለቅን አሳባችን ለምን ሰዎች ክፉ ነገር ይመልሱልናል?” በማለት ሲጠይቁ ይሰማል፡፡ ለቅን አሳባችን ከዓለም ዘንድ ተቃራኒ ነገር እንደሚጠብቀን ለመረዳት ዓለም የሚወደው የገዛ

ወገኑን ነው” የሚለውን የጌታችንን ትምህርት ልብ ይሏል፡፡ በዘመናችን አሳልፈው ሊሰጡን የሚፈልጉ ሰዎች ፈታኝ ጥያቄ እንደሚያቀርቡልንም ከወዲሁ ልንገነዘብ ይገባል፡፡

 ረቡዕ

በቅዱስ ማቴዎስና በቅዱስ ማርቆስ አመዘጋገብ መሠረት በዕለተ ረቡዕ የሚከተሉት ሦስት ነገሮች ተፈጽመዋል፡-

አንደኛ፡- የካህናት አለቆች፣ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ  ተማክረዋል፤ ሁለተኛ ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ አንዲት የተጸጸተች ሴት ሽቱ ቀብታዋለች፡፡ ሦስተኛ ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያንና ከካህናት አለቆች ዘንድ ሠላሳ ብር ለመቀበል ተስማምቷል፡፡

የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሹማምት በጌታችን ላይ ይሙት በቃ ለመወሰን የሰበሰቡት ሸንጐ በአብዛኛው የተሰየሙት ሰዱቃውያን ሲኾኑ ሌሎቹ ደግሞ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ነበሩ፡፡ ሸንጐው በአጠቃላይ ሰባ ሁለት አባላት የነበሩት ሲኾን የሚመራውም በሊቀ ካህናቱ በቀያፋ ነበር፡፡ በዕለቱ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት ይዘው እንደሚገድሉት አይሁድ በዚህ ሸንጎ መክረዋል፡፡

ከዳተኛው ይሁዳም ጸሐፍት ፈሪሳውያንና የካህናት አለቆች በጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ላይ የነበራቸውን ጥላቻ ያውቅ ስለነበር ምን ትሰጡኛላችሁ? እኔም አሳልፌ እሰጣችኋለሁ”  በማለት ጌታችንን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ተስማምቷል (ማቴ.፳፮፥፲፭)፡፡

የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተምር በነበረበት ወቅት ከምእመናን ለሚገባው ገንዘብ ሰብሳቢ (ዐቃቤ ንዋይ) ነበር፡፡ ከሚሰበሰበው ሙዳየ ምጽዋት ለግል ጥቅሙ እየቀረጠ የማስቀረት የእጅ አመል ነበረበት፡፡ ይሁዳ ፍቅረ ንዋይ እንደሚያጠቃው ድብቅ አመሉ ጎልቶ የወጣው ጌታችን በለምጻሙ በስምዖን ቤት ሳለ አንዲት ሴት ዋጋው ውድ የኾነ ሽቱ በቀባችው ጊዜ ነው፡፡ በዚያች ዕለት ይሁዳ የተቃውሞ ድምፅ አሰምቶ ነበር፡፡

ይህ ሽቱ ተሽጦ ለድሆች ቢሰጥ መልካም ነበር” በማለት ያቀረበው አሳብአዛኝ መሳይ ቅቤ አንጓች እንደሚባለው ነበር፡፡ ሽቱ ሲሸጥ የሚያገኘው ጥቅም አለ፤ ሽቶው በጌታችን እግር ሥር ከፈሰሰ ለእርሱ የሚተርፈው የለም፡፡ ይሁዳ ተቆርቋሪ መስሎ ያቀረበው አሳብ ተቀባይነት በማጣቱም ማኩረፊያ ያገኘ መስሎት በቀጥታ ከካህናት አለቆች ዘንድ ሔዶ ጌታንን በሠላሳ ብር ለመሸጥ ተዋዋለ፡፡ ይህ ታሪክም በሦስቱ ወንጌላት ውስጥ በሚከተሉት ምዕራፎች ተመዝግቦ እናገኛዋለን፡፡ (ማቴ. ፳፮፥፫-፲፮፤ ማር. ፲፬፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፪፥፩፮)፡፡

የአስቆሮቱ ይሁዳ እንደ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ተምሯል፡፡ በረከተ ኅብስቱን ተመግቧል፡፡ ልዩ ልዩ ተአምራት በጌታችን እጅ ሲደረጉ ሁሉ ተመልክቷል፡፡ ጌታችንም ከሌሎች ሐዋርያት ሳይለየው እግሩን አጥቦታል፡፡ ከዳተኛው ይሁዳ ግን ለሐዋርያነት የጠራውን፣ ተንበርክኮ እግሩን ያጠበውን ጌታ ለሞት አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሔዳል፤ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት!” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፳፮፥፳፬)፡፡

ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ዘንድ ፍቅሩን ገንዘብ ሲያደርጉ ይሁዳ ግን ርግማንን ነው ያተረፈው፡፡ ገንዘብ የኃጢአት ሥር ነው ተብሎ እንደ ተነገረ የኃጢአት ሥር የተባለው ገንዘብ የክርስቲያኖችን ሕይወት ያዳክማልና ምእመናን እንደ ይሁዳ በገንዘብ ፍቅር እንዳንወድቅ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ሰው ይህን ዓለም ቢያተርፍ ነፍሱን ከጐዳ ምን ይጠቅመዋል?” ተብሎ የተነገረውን ቃል ልብ ማለት ጠቃሚ ነው፡፡

ክርስቲያን ነን በማለት የክርስትናውን ስም ብቻ በመያዝ እምነታቸውን፣ በገንዘብ የሚለውጡ ሰዎች ዛሬም እንደ ይሁዳ ጌታችንን እየሸጡት እንደ ሆነ ሊገነዘቡት ይገባል፡፡ ለድሆች መመጽወት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ዳሩ ግን በድሆች ስም የሰውን ገንዘብ ለግል ጥቅም ማዋል እጅግ የከፋ ኃጢአት ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለገንዘብ ብለው ድሆችን ለረኃብ ለችግር ባልንጀራቸውን ለመከራ እና ለሞት አሳልፈው ሲሰጡ ምንም አይጸጽታቸውም፡፡ እውነተኛ ክርስቲያኖች ግን ሕይወታችንን ለገንዘብ ፍቅር ሳይሆን ለእምነታችንና ለባልንጀራችን አሳልፈን መስጠት ይኖርብናል፡፡ በፍቅረ ንዋይ ተጠምደን ሰዎችን አሳልፎ በመስጠት ለአይሁዳውያን ሸንጐ ምቹ ሆነን መገኘት እንደማይገባ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡ስምዐ ተዋሕዶ ልዩ ዕትም ዘሰሙነ ሕማማት

ሆሳዕና በአርያም

ሆሳዕና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ሕዝቡ በተለይም አእሩግና ሕፃናት “ሆሳዕና ለዳዊት ልጅ፣ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፣ ሆሳዕና በአርያም” በማለት ጌታችንን በክብር መቀበላቸው የሚታወስበት በዓል ነው፡፡

ሆሳዕና የሚለው ቃል በዕብራይስጥ “ሆሼዕናህ” የሚል ትርጉም ሲኖረው “እባክህ አሁን   አድን” ማለት ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በመዝሙሩ “ኦ እግዚኦ አድኅንሶ፤ ኦ እግዚኦ ሠርሕሶ፤ ብሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ አቤቱ እባክህ አሁን አድን፣ አቤቱ እባክህ አሁን አቅና፣ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩከ ነው” እያለም ዘምሯል፡፡ (መዝ.፩፻፲፯፥፳፭-፳፮)፡፡  ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን መነሻ በማድረግ ሆሳዕና የሚለውን ስያሜ ለዐቢይ ጾም ስምንተኛ ሳምንት ሰጥታ ታከብረዋለች፡፡ ስያሜውንም ያገኘው በዕለቱ ከሚዘመረው መዝሙር ነው፡፡

ዕለቱን በተመለከተ የተለያዩ ምሳሌዎች ይመሰላሉ፡-

የጸበርት እሑድ /Palm Sunday/፡-

ይህ ዕለት የጸበርት እሑድ ይባላል፡፡ ታሪካዊ አመጣጡ ከደገኛው አባታችን ይስሐቅ ልደት ጋር ተያይዞ የመጣ ነው፡፡ የመልካም ምኞትና የድል አድራጊነት መገለጫም ነው፡፡ እናታችን ሣራ ልማደ እንስት ከተቋረጠባት በኋላ በእርግና ዘመኗ ሁሉን ቻይ የሆነ አምላክ ይስሐቅን በሰጣት ጊዜ ዘመዶችዋ የጎበኛትን አምላክ ለማመስገንና የተሰማቸውን ደስታ ለመግለጽ የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ ጠይቀዋታል፡፡

የዮዲት አሦራውያንን ድል ማድረግ፡-

የአሦር ንጉስ ናቡከደነፆር እስራኤልን ለመውረር፣ ሀገሪቱንም ለማጥፋትና ለመበርበር ተነሣ፤ የጦር ቢትወደዱን ሆሎፎርኒስን ልኮ ያጠፋቸው ዘንድ ወሰነ፡፡ ሆሎፎርኒስም የጌታውን ትእዛዝ ይፈጸም ዘንድ ሀገሪቷንም ይበዘብዛት ዘንድ ሠራዊቱን አስከትሎ በእስራኤል ላይ ዘመተ፡፡

ዮዲትም ወሬውን በሰማች ጊዜ በራሷ ላይ አመድ ነስንሳ፣ ማቅ ለብሳ ጸለየች፡፡ ጸሎቷንም በጨረሰች ጊዜ የመበለትነትዋን ልብስ ለበሰች፤ ጌጣ ጌጦችዋንም አጥልቃ ወደ ሆሎፎርኒስ ቀረበች፡፡ በደም ግባቷም ተማረከ፣ ግብዣም አደረገላት፡፡ ከመጠን በላይ ጠጥቷልና ራሱን በሳተ ጊዜ በራሱ ሰይፍ አንገቱን ቆረጠች፤ በግንብ ጫፍ ላይ እንዲሰቅሉትም አደረገች፤ አሦራውያንም በሽንፈት ተመለሱ፡፡

የእስራኤል ሴቶችም ዝናዋን ሰምተዋልና “ያይዋትና ይመርቋትም ዘንድ ወደ እርሷ ሮጠው ተሰበሰቡ፤ ታላቅ በዓልንም አደረጉላት፤ ዘንባበውንም በእጇ ያዘች፤ ከእርሷ ጋር ላሉት ሴቶች ሰጠች፡፡ በሕዝቡም ፊት ሴቶችን ሁሉ እየመራች በዝማሬ ሄደች፤ የእስራኤልም አርበኞች ሁሉ የጦር መሣሪያቸውን ከዘንባባ ጋር ይዘው እየዘመሩ ተከተሏት” እንዲል፡፡ (ዮዲ. ፲፭፥፲፩-፲፬)፡፡

በሐዲስ ኪዳንም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ላይ ሆኖ ሕፃናትና አእሩግ “ለዳዊት ልጅ መድኀኒት መባል ይገባዋል” (የማቴ. ወንጌል አንድምታ) እያሉ ዘንባባ ይዘው ሲዘምሩ ኦሪትንና ትንቢተ ነቢያትን በሚገባ እንከተላለን ይሉ የነበሩ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ግን “መምህር ሆይ ደቀ መዛሙርትህን ገሥጻቸው” ብለውታል፡፡ ጌታችንም መልሶ “እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ” ሲል መልሶላቸዋል፡፡

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ በነቢዩ ዘካርያስ እንዲህ ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ፡፡ “እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም፣ በአህያዪቱ ግልገል በውርንጫዪቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፡፡” እንዲል (ዘካ.፱፡፱)፡፡

ጌታችን በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱ የሰላም ንጉሥ መሆኑን ያመለክታል፡፡ እስራኤል ዘመነ ምሕረት ሲሆንላቸው አባቶቻቸው በአህያ ጀርባ ተቀምጠው ይታዩ ነበር፡፡ ጌታም እውነተኛ የኅሊና ሰላም ይዤላችሁ መጣሁ ሲል በአህያ ጀርባ ወደ ቤተ መቅደስ ተጉዟል፡፡ (ማቴ.፳፩፥፬፤ ማር.፲፩፥፩-፲፤ሉቃ.፲፱፡፳፷-፵፤ ዮሐ.፲፪፤፲፭)፡፡

፩. አህያዋና ውርንጫዋ፡- 

በዚህ ዓለም አህያ ለሸክም የሚያገለግል፣ የተናቀ፣ ነገር ግን ትሑት የሆነ እንስሳ ነው። ከዚህ በተጨማሪም አህያ እንደ በቅሎ ሰጋር እንደ ፈረስ ፈጣን አይደለም። በአህያ የተቀመጠ ሰውም አሳድዶ አይዝም፤ ጋልቦ ሮጦም አያመልጥም። ተሸክሞ እንኳን በዱላ እየተደበደበ አህያ ጌታውን በቅንነት ያገለግላል። ጌታችን በዚህች ትኁት በሆነችው አህያ መገለጡ በትኁታን ለማደሩ ምሳሌ ነው።

ጌታችን የተቀመጠባቸው አህዮች አንደኛዪቱ ጭነት የለመደች ውርንጫይቱ ደግሞ ገና ያልለመደች ናት። አህያይቱ የኦሪት ምሳሌ ስትሆን ቀንበር መሸከም መቻሏ ሕገ ኦሪትን መጠበቅ የለመዱ የእስራኤል ዘሥጋ፣ ውርንጫዪቱ ደግሞ ቀንበር መሸከም የማትችል ስትሆን የአሕዛብ ምሳሌ ናት። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን በሁለቱም ተቀምጦባቸዋል። አህያይቱ ቀንበር መሸክም የለመደች እንደሆነች ሁሉ ኦሪትም ሕግ ናትና፤ ውርንጫይቱ ቀንበር መሸክም ያልለመደች እንደሆነች ወንጌልም ያልተለመደች ሕግ ናትና፡፡ (ወንጌል አንድምታ)፡፡

ልብስ:- 

ደቀ መዛሙርቱ አህያዪቱን ከነውርንጫዋ ከታሰረችበት ቦታ ፈትተው እንዳመጡለት በዚያ የነበሩት ሰዎች ልብሳቸውን በአህያዪቱና በውርንጫዪቱ ጀርባ ጎዘጎዙ፤ አህያዪቱ ተራምዳ በምትሄድበት መንገድ ሁሉ ልብሳቸውን አነጠፉ። ይኽም ምሳሌ ነው። ልብስ የውስጥ ገመናን ሸፋኝ ነው። አንተ ገመናችንን ከታች ነህ ሲሉ ልብሳቸውን ጎዘጎዙለት። በሌላ በኩልም ልብስ ክብር ነው፤ ያንን የሚያስከብረውን ልብስ አነጠፉለት። ክብራችን አንተ ነህ ሲሉ ክብራቸውን ዝቅ አደረጉለት። እግዚአብሔር በረድኤት ሲያድርብን ይንቁን ያንገላቱን የነበሩት ሁሉ ያክብሩናል። ቅዱሳን በዚህ ዓለም ሲኖሩ ብዙ መከራ ተፈራርቆባቸዋል። ዓለም ትቢያና ጉድፍ አድርጓቸዋል። ይኹን እንጂ በሃይማኖታቸው ጽናት በምግባራቸው ቅናት እግዚአብሔር አድሮባቸው ሁሉ ያከብራቸዋል። አስጨናቂዎቻቸውን ሳይቀር ይገዙላቸዋል።

ጌታችን በቤተ መቅደስ፡-

 ሕዝቡም በብዙ ምስጋናና እልልታ ልብሳቸውን በመንገድ ላይ እያነጠፉ፤ ሌሎችም ከዛፎች ጫፍ ጫፉን እየቆረጡ በመንገድ ላይ ያነጥፉ ነበር፡፡ ይልቁንም ሽንገላ ከሌለበት ከሕፃናት አፍ የሚፈልቀው ምስጋና እየቀረበለት በልዩ ግርማ ጌታችን በኢየሩሳሌም አደባባይ አቋርጦ ወደ ቤተ መቅደስ ገባ።

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህች ምድር በሥጋ ተገልጦ እየተመላለሰ ባገለገለባቸው ዓመታት ውስጥ ከተቆጣባቸው ጥቂት ጊዜያት አንዱ በሆሳዕና ዕለት ወደ ቤተ መቅደሱ ሲገባ ነው። የጸሎት ቤት የሆነችውን የእግዚአብሔር ቤት አይሁድ የገበያ ቦታ የቅሚያና የዝርፊያ አደባባይ አደረጓት። በዚህም ትሑቱ ጌታ ተቆጣ። በዚያ ይሸጡ ይለውጡ የነበሩትን አስወጣቸው። ወንበራቸውን ገለበጠው። ቤቱን ቀደሰው። “ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል” እንዲል ቅዱስ ዳዊት። አነፃው፤ ለየው፤ አከበረው፤ ወደ ቀድሞ ክብሩ መለሰው። ይኽን ቤት ነገረ ምፅአቱን ለደቀ መዛሙርቱ ባስተማረበት ወቅት ትቶት ሄዶ ነበር። “ጌታችን ኢየሱስ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ሄደ” እንዲል ቅዱስ ማቴዎስ። የሆሳዕና ዕለት ግን ለሐዲስ ኪዳን አገልግሎት እንዲሆን ነጋዴዎቹን አጭበርባሪዎቹን አውጥቶ አጽድቶ ሰጠን። በዚያም በተቀደሰው ቤተ መቅደስ “በቤተ መቅደስም ዕውሮችና አንካሶች ወደ እርሱ መጡ፤ አዳናቸውም” ተብሎ እንደ ተጻፈው። ማቴ ፳፩፣ ፲፬።

የሊቃነ ካህናትና የጸሐፍት መቆጣት፡-

የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ ክቡር በሆነ ምስጋና መመስገን፣ የቤተ መቅደሱ በክርስቶስ መጽዳትና ወደ ቀደመ ክብሩ መመለስ ሊቃነ ካህናትንና ጸሐፍቱን አላስደሰታቸውም። በክፋትና በተንኮል ካባ እንደተጀቦኑ ጻድቃን መስለው ለዘመናት ትሑትና የዋህ የሆነውን ሕዝበ እግዚአብሔር ሲያታልሉ የነበሩት እነዚህ አካላት በጽድቁ ክፋታቸውን የሚገልጥባቸው የክርስቶስ በክብር መገለጥ እንዲሁም መመስገን አስቆጣቸው። የእርሱ መገለጥና መመስገን እነርሱን የሚያሳንስ ክፋታቸውን የሚገልጥ መሆኑን ተረዱት። ጌታችን በወንጌል “ሥራው ክፉ የሆነ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፤ ክፉም ስለሆነ ሥራው እንዳይገለጥበት ወደ ብርሃን አይመጣም (ዮሐ. ፫፣፳)” እንዳለው ሆነባቸው።

ትቶአቸው ሄደ፡-

የታሰሩትን ፈትቶ ወደ ቤተ መቅደስ አስገብቶ፣ ቤተ መቅደሱንም ባርኮ ፈውስ በረከት አሳድሮበት፣ ተመስግኖበት ለዘላለምም የሚመሰገንበት መሆኑን ለተቃወሙት አስረድቶ ሲያበቃ “ትቶአቸው ከከተማው ወደ ቢታንያ ሄደ። በዚያም አደረ፡፡” ክህነታቸውም አለፈች። ያላቸውን ክብር፣ ሀብት፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ ቅንና ትሑት ልቡና ለነበራቸው ለሐዋርያት ተሰጠች።

በአጠቃላይ በዓለ ሆሳዕና በዚህን ቀን አህዮቹ ከጌታችን የተላኩላቸውን ፈቺዎቻቸውን (ደቀ መዛሙርቱን) አላስቸገሯቸውም። እንደ ልቧ መቦረቅ የምትወድ ውርንጫ እንኳን አደብ ገዝታ ፈቺዎቿን ተከትላ ሄደች። እኛስ? ከታሰርንበት የክፋትና የኃጢአት ሁሉ ማሰርያ መች ይሆን የምንፈታው?  እንግዲህ እንደዚያን ዕለት ሰዎች ልብሳችንን ሳይሆን ልባችንን፣ የዛፍ ቅርንጫፍ ሳይሆን ራሳችንን በጌታችንና የእርሱ እውነተኛ አገልጋዮች በሆኑ በቅዱሳኑ ፊት ዝቅ እናድርግ። ለዚህም የልዑል እግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሁሉ ተራዳኢነት አይለየን። አሜን።

ደብረ ዘይት

መ/ር በትረ ማርያም አበባው

ደብረ ዘይት ማለት የወይራ ተራራ፣ የወይራ ዛፍ የሚበዛበት ተራራ ማለት ነው። ቅዱስ ያሬድ ለዐቢይ ጾም ሰንበታት ስያሜ ሲሰጥ አምስተኛውን እሑድ ደብረ ዘይት ብሎታል። በዚህም ተራራ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዳግም ምጽአቱና ምልክቶቹ ለቅዱሳን ሐዋርያት ነግሯቸዋል።

በዚህ የዐቢይ ጾም አምስተኛው እሑድ ላይ በስፋት የሚነገረውና በሥርዓተ ማኅሌቱም የሚቆመው ዳግም ምጽአትን የሚያወሳ ጉዳይ ነው። “ወእንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ቀርቡ ኀቤሁ አርዳኢሁ እንተ ባሕቲቶሙ ወይቤልዎ ንግረነ ማእዜ ይከውን ዝንቱ ወምንት ተአምሪሁ ለምጽአትከ ወለኅልቀተ ዓለም፤ ያን ጊዜ ጌታ በደብረ ዘይት ሳለ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው እንዲህ አሉት፡- ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለሙ ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድነው?” ብለው ጠይቀውታል። (ማቴ. ፳፬፣፫)

 ምጽአት ምንድን ነው?

በመጽሐፍ ቅዱስ የትርጓሜ ስልት ምጽአት እንደ ጊዜ ግብሩ ይተረጎማል፡፡ ለምሳሌ፡- “እግዚአብሔርሰ ገሀደ ይመጽእ” (መዝ. ፵፱፣፩) የሚለውን ብንመለከት በሦስት መንገድ ሲተረጎም እናገኘወለን፡፡ አንደኛው እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል ሲል ረድኤት ይሰጣል ተብሎ ይተረጎማል። ሁለተኛው እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል ሲል የማይታየው ረቂቁ አምላክ ሥጋን ተዋሕዶ ይታያል ማለት ነው። ሦስተኛው እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል ሲል ዓለምን ለማሳለፍ በኃጥኣን ሊፈርድባቸው ለጻድቃን ሊፈርድላቸው ይመጣል ማለት ነው።

ከምጽአት በፊት የሚታዩ ምልክቶች

. ብዙዎች በሐሰት እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ ይመጣሉ (ማቴ. ፳፬፭ )፡-

ይህን የመሰለ በዓፄ ዘድንግል ዘመነ መንግሥት በአማራ ሳይንት እኔ ክርስቶስ ነኝ ብሎ ተነሥቶ ነበር። ንጉሡም “እስመ ይትነሥኡ ሐሳውያነ መሲሕ፣ ወሐሳውያነ ነቢያት፣ ወይገብሩ ተአምራተ ወመንክራተ ዐበይተ ለአስሕቶ፤ ሐሳውያን ነቢያት፣ ሐሳውያን መምህራን ይነሳሉ፤ ሰውን ያስቱ ዘንድ ጽኑ ጽኑ ተአምራትን ያደርጋሉ።” እንዲል (ማቴ. ፳፬፣፳፬) ድፍረት የተሞላበትን ትምህርቱንና ሐሳዊነቱን ተረድተው አስገድለውታል፡፡

ተአምርን ኃጥኣንም ጻድቃንም ሊያደርጉት ይችላሉ። በሙሴ ዘመን የነበሩ ጠንቋዮችም ተአምር ሠርተዋል። ሊቀ ነቢያት ሙሴም ተአምር ሠርቷል።

ስለዚህ ተአምር ብቻ ዓይተን አንከተልም። መንፈሳዊ ሕይወቱ በምልአት ተጠንቶ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የሚመራ ከሆነ አስተምህሮውም ትክክል ከሆነ እንጂ ተአምር ብቻ ስላደረገ አንድ ሰው ትክክል ነው አይባልም። እንግዲህ በድፍረት እኔ ክርስቶስ ነኝ የሚል ሐሳዊ መሲሕ እንደሚመጣ፣ የክርስቶስ ያልሆኑ ነገር ግን የክርስቶስ ነን ብለው የሚመጡ ሐሰተኛ መምህራንም እንደሚነሡ ይነግረናል።

. ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥት በመንግሥት ላይ ይነሣል (ማቴ. ፳፬፯)፡-

አንዱ ሕዝብ ሌላውን ሕዝብ ይጠላዋል፤ አንዱ መንግሥት ሌላውን መንግሥት ይጠላዋል። ይህማ ቀድሞስ ነበረ አይደለምን ቢሉ በዝቶ ይደረጋል ማለት ነው።

. ረኀብ፣ ቸነፈር ይመጣል (ማቴ. ፳፬፱)፡-

ያን ጊዜ ለጸዋትወ መከራ አሳልፈው ይሰጧችኋል፣ ይገርፏችኋል፣ ይገድሏችኋል፣ ይጠሏችኋል። በእኔ ስም ስላመናችሁ በሰው ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ። ይህ ለጊዜው ለቅዱሳን ሐዋርያት የተነገረ ቢሆንም ፍጻሜው ግን እስከ ዕለተ ምጽአት ለሚነሡ ክርስቲያኖች ነው።

. ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ይስታሉ (ማቴ. ፳፬፲)፡-

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው “ሃይማኖት አንዲት ናት” (ኤፌ. ፬፣፬)፡፡  ይህ ሆኖ ሳለ ግን ሰይጣን በዘራው ኑፋቄ፣ ከመጻሕፍት ያላገኙትን፣ ከመምህር ያልተማሩትን፣ በልብ ወለድና በመሰለኝ የቅዱሳት መጻሕፍትን ቃል እንደ ቃሉ ሳይሆን ለራሳቸው ስሜት እንዲስማማ እየተረጎሙ ብዙዎች ከአንዲቱና ርትዕት ከሆነችው ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ተለይተዋል። ብዙዎች በሃይማኖታቸው ይስታሉ በማለት በሃይማኖት የሚጸኑት ጥቂቶች መሆናቸውን ይነግረናል።

. ፍቅር ትቀዘቅዛለች (ማቴ. ፳፬፲፪)፡-

የሕገ እግዚአብሔር ፍጻሜው ፍቅር ነው። ሕግጋት በሙሉ ፍቅረ እግዚአብሔርና ፍቅረ ቢጽ ተብለው ይከፈላሉ። የፍቅረ እግዚአብሔር መገለጫው ሕጉን ትእዛዙን መጠበቅ ነው። “ዘያፈቅረኒ ይዕቀብ ቃልየ፤ የሚወደኝ ቃሌን ይጠብቅ” ብሏል (ዮሐ. ፲፬፣፳፪)፡፡ የፍቅረ ቢጽ መገለጫው ደግሞ ሊደረግብን የማንፈልገውን እና ለእኛ የማንመኘውን በሌላው አለማድረግና አለመመኘት ሲሆን ለእኛ ሊደረግልን የምንፈንገውንና የምንመኘውን ደግሞ ለሌላውም ማድረግና መመኘት ነው። “ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ” ዘሌ.፲፱፣፲፰ ይላልና”።

በመጨረሻው ዘመን ግን ፍቅር ትቀዘቅዛለች። ራስ ወዳድነት ይበዛል ማለት ነው። “ወዘንተ ባሕቱ አእምር ከመ በደኃሪ መዋዕል ይመጽኣ ዓመታት እኩያት። ወይከውኑ ሰብእ መፍቀርያነ ርእሶሙ ባሕቲቶሙ ወመፍቀርያነ ፈጊዕ ወንዋይ፤ በመጨረሻው ዘመን ክፉ ዘመናት እንደሚመጡ ዕወቅ። ሰዎች ራሳቸውን ብቻ የሚወዱ ይሆናሉ። ገንዘብን ወዳጅ ይሆናሉ” ተብሏል። (፪ኛ ጢሞ .፫፣፩-፫)፡፡

ምጽአት መቼ ይሆናል?

ዳግም ምጽአት መቼ እንደሚሆን አይታወቅም። ምጽአት መቼ እንደሚሆን የሚያውቀው ፈጣሪ ብቻ ነው፡፡ “ወበእንተሰ ይእቲ ዕለት ወኪያሃ ሰዓት አልቦ ዘየአምራ፤ ያችን ሰዓት ያችን ዕለት የሚያውቃት የለም፡፡” (ማቴ. ፳፬፣፴፮) እንዲል የሰው ልጅ ምጽአት መቼ እንደሚሆን ሰለማያውቅ መልካም ሥራን እየሠራ ተግቶ እንዲጠብቅ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሯል፡፡ በኋላም “ድልዋኒክሙ ሀልው፤ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ” ብሎናል። ስለዚህ ንስሓ ገብተን፣ ሥጋውን ደሙን እየተቀበልን መልካም ሥራን እየሠራን ፈጣሪያችንን እንጠብቀው።

ፍርድ በምጽአት

መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት በምጽአት “ለሁሉ እንደ ሥራው ትከፍለዋለህ” (መዝ. ፷፪፥፲፪)  ብሎ እንደተናገረው እግዚአብሔር ለሁሉ እንደሚገባው እንደ ሥራው ፍርድ የሚሰጥ ያን ጊዜ ነው። “አሜሃ ይብሎሙ ንጉሥ ለእለ በየማኑ ንዑ ኀቤየ ቡሩካኑ ለአቡየ ትረሱ መንግሥተ ሰማያት ዘድልው ለክሙ እምቅድመ ይትፈጠር ዓለም፤ እናንተ የአባቴ ቡሩካን ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥተ ሰማያትን ውረሱ” በማለት መልካም ሥራ የሠሩትን በቀኙ ያቆማቸዋል። (ማቴ. ፳፭፣፴፬)።

ሕይወታቸውን በከንቱ ያሳለፉ፣ ከመልካም ሥራ ርቀው ሲቀጥፉና ሲበድሉ፣ ለክፉም ሲተባበሩ ለነበሩት ኃጥኣን ደግሞ “ሑሩ እምኔየ ርጉማን ውስተ እሳት ዘለዓለም ዘድልው ለሰይጣን ወለመላእክቲሁ፤ እናንተ ርጉማን ለሰይጣንና ለሠራዊቱ ወደተዘጋጀው የዘለዓለም እሳት ሒዱ” ይላቸዋል፤ በግራውም ያቆማቸዋል።

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ለእያንዳንዱ የዐቢይ ጾም ሰንበታት ስያሜ ሰጥታ የምታስተምር ሲሆን አምስተኛውን የዐቢይ ጾም ሰንበት ደብረ ዘይት (ዕለተ ምጽአት) በማለት ሰይማዋለች፡፡ በዕለቱም ከዋዜማው ጀምሮ የሚዜመው ዜማ፣ የሚነበቡት ምንባባት፣ የሚሰበከው ስብከት ሁሉ ዕለቱን የተመለከቱ ናቸው፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።