የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ

መ/ር ሕሊና በለጠ
ክፍል ሁለት
የሞቱና የትንሣኤው ፍሬ ነገሮች
ጌታችን በመስቀል ላይ ሲሞት ድኅነታችን ተከናወነ፣ ሞትን ድል አድርጎ ሲነሣ ደግሞ ትንሣኤያችን እውን ሆኖ ተገለጠ፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የማይቋረጥ አገልግሎት መሠረት የሆነ ድል፣ የምድርም የደስታዋ ምንጭ ሆነ፡፡ “ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ ተሐፂባ በደመ ክርስቶስ፤ በክርስቶስ ደም ታጥባ ምድርም ደስታን ታደርጋለች” በማለት ሊቁ ቅዱስ ያሬድ እንደገለጸልን እኛም ደስታችንን ለመግለጽ እናመሰግናለን፡፡
ከነገረ ድኅነት አንጻር የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ያመጣውን ውጤት በሦስት ከፍለን እንመልከት፡
ሀ. በሲኦልና በሞት ላይ የተገኘ ድል
የሰው ልጅ ገነትን ካጣ በኋላ ኑሮው በሁለት የተከፈለ ነበር፡፡ የምድር ሕይወቱ እና ከሞት በኋላ የሚኖረው ሕይወቱ፡፡
የምድር ሕይወቱ ነፍሱ ከሥጋው ስትለይና የሥጋ ሞትን ሲሞት ያበቃል፡፡ ከዚያም ገነት የተዘጋች ናትና ነፍሱ ወደ ሲኦል ትሔዳለች፡፡ ሲኦል ደግሞ በጽልመትና በስቃይ የተሞላ፣ እንዲሁም የጨለማው ገዢ ዲያቢሎስ የሠለጠነበት ሥፍራ ነው፡፡ መዝሙረኛው ቅዱስ ዳዊት “በሞት የሚያስብህ የለምና፥ በሲኦልም የሚያመሰግንህ ማን ነው?” (መዝ.፮፥፭) ሁሉም የጌታችንን መምጣት፣ መሞትና መነሣትን በታላቅ ተስፋ የሚጠብቅ ነበር፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ይህንን ሲገልጽ “እነዚህም ሁሉ በእምነታቸው ተመስክሮላቸው ሳሉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አላገኙም፥ ያለ እኛ ፍጹማን እንዳይሆኑ እግዚአብሔር ስለ እኛ አንዳች የሚበልጥ ነገርን አስቀድሞ በይኗልና” ብሏል፡፡ (ዕብ.፲፩፥፴፱-፵)፡፡
ጌታችን፣ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ለእኛ ሲል ከሞተ በኋላ በአካለ ሥጋ ወደ መቃብር ሲወርድ፣ በአካለ ነፍስ ደግሞ ወደ ሲኦል ወርዶ ነበር፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ይህንን ምሥጢር እንዲህ ይዘክረዋል፡- “ነፍሱን ከሥጋው በለየ ጊዜ፡ ያን ጊዜ በሲኦል ፈጥኖ ብርሃን ታየ፡፡ ጌታችን በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሔደ፡፡ ሲኦል ተነዋወጠች፤ መሠረቶቿም እፈርስ እፈርስ አሉ፤ ምድርን ያለ ጊዜዋ እንዳታልፍ አጸናት፤ ደሙን በምድር ላይ አፈሰሰ፡፡ ከኅልፈት ጠበቃት፤ በርሷ ያለውንም ሁሉ ጠበቀ፡፡ ስለ ፍጥረት ሁሉ ሥጋውን በመስቀል እንደተሰቀለ ተወው፡፡ ነፍሱ ግን ወደ ሲኦል ወረደች፤ ከዚያ ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን አዳነች፤ ሲኦልንም በዘበዘች፤ ፍጥረትንም ሁሉ ገንዘብ አደረገች፡፡ ሥጋውም በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡” እያለ በዕለተ ዐርብ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምና ልጆቹን ለማዳን በመስቀል ላይ የከፈለውን ዋጋ ያሳየናል፡፡
ለዘመናት በሞት ጥላ ውስጥ ሆነው በተስፋ ሲጠብቁት ለነበሩት ነፍሳት ሁሉ በሲኦል ውስጥ ድኅነትንና ሰላምን ሰበከላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ይህን ሲነግረን “ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር እንዲያቀርበን እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኃጢአት ምክንያት ሞቶአልና፤ በሥጋ ሞተ፣ በመንፈስ ግን ሕያው ሆነ፥ በእርሱም ደግሞ ሄዶ በወኅኒ ለነበሩ ነፍሳት ሰበከላቸው” (፩ጴጥ.፫፥፲፰-፲፱) አለ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ስለዚሁ ጉዳይ ሲናገር “ምርኮን ማርከህ ወደ ሰማይ ወጣህ፤ ጸጋህንም ለሰው ልጅ ሰጠህ” ይላልና ከምድር በታች (ሲኦል) ካልወረደ መውጣቱ ምንድን ነው? የወረደው እርሱ ነው፤ ሁሉንም ይመላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ደግሞ እርሱ ነው” ሲል ገልጾታል፡፡ (ኤፌ.፬፥፰-፲)፡፡
ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዘቆጵሮስ የዘመነ ብሉይ ሰዎችን ጩኸት እግዚአብሔርም እንደሰማቸውና፣ መለኮት ከሥጋ ጋር በመቃብር ከነፍስም ጋር በሲኦል በተዋሕዶ እንደ ነበር ሲያስረዳ “ነቢይ ዳዊትም ነፍሴን በሲኦል አትተዋትም፤ የባሕርይ ልጅህንም ሙስና መቃብርን ያይ ዘንድ አሳልፈህ አትሰጠውም አለ፡፡ ይህም ጌታ በተዋሐደው አካል ያለውን የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ያስረዳል፤ የቀና ልቡና ዕውቀት በእርሱ ጸንቶ ይኖር ዘንድ፡፡ ዳዊት እንደተናገረው እውነት ሆነ፤ ነፍስ መለኮትን ተዋሕዳ ወደ ሲዖል ወርዳለችና፤ ሥጋም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ሳለ መለኮት ከሥጋ አልተለየም” ብሏል፡፡
ይህ ሁሉ የሚያስረዳው በማኅፀነ ማርያም መለኮት ከትስብእት፣ ትስብእት ከመለኮት ጋር ከተዋሐደ በኋላ ምንም ዓይነት መለያየት ሳይኖር መለኮት በሥጋ እየተሰደደ፣ እየደከመ፣ እየተራበ፣ እየተጠማ፣ እየታመመ፣ እንዲሁም በመስቀል ተሰቅሎ በሞቱ ዓለምን ያዳነ መሆኑን ነው፡፡ ከላይ የሆኑት ሁሉ መለኮት በሥጋ ብለን የምንገልጸው ሲሆን እንዲሁ ሥጋም በመለኮት ሕሙማንን እየፈወሰ፣ ዕውራንን እያበራ፣ የተራበ እያበላ፣ ሙት እያነሣ፣ የተፈጸመ የነገረ ድኅነት ጉዳይ እንደሆነ ነው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም በትንሣኤ በዓል ድርሳኑ “ሲኦል ወደዚያ በወረደው በክርስቶስ ምርኮ ሥር ሆነ፤ ተበረበረ” ሲል ገልጾታል፡፡
ሲኦልን መበዝበዙን ቅዱስ ቄርሎስ ዓምደ ሃይማኖት “ታመመ፤ ሞትን ከተቀበለበት ከሥጋ ጋር ተዋሕዶ በመስቀል ላይ በፈቃዱ ለሥጋውያን ሞተ፤ ባሕርየ መለኮት ሥጋን ተዋሕዶ በማኅፀን ካደረ ጀምሮ ሥጋ ገንዘቡ እንደ መሆኑ በሥጋ ይኸንን ሥርዓት ፈጸመ፡፡ ለማይመረመር ለመለኮቱ ባሕርይ እንደሚገባ ደግሞ እርሱ ኅብስት አበርክቶ ሁሉን ያጠግባል፤ አይራብም፤ አይጠማም፤ አይደክምም፤ አያንቀላፋም፤ አይታመምም፤ አይሞትም፤ ሕይወትን ለሁሉ ይሰጣል፡፡ ዳግመኛ በዚያ በሲኦል ተገዝተው ያሉ ነፍሳትን ያድን ዘንድ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወረደ፤ በመለኮቱም ሲኦልን በዘበዘ” ብሎ አስተምሯል፡፡
አስቀድመን በሰፊው እንዳየነው ከክርስቶስ ትንሣኤ በኋላ ሞት አስፈሪነቱ ጠፋ፡፡ ሞት ከምድራዊው ሕይወት የሚያርፉበት ዕረፍት፣ ወደ ሰማያዊው ሕይወት መሸጋገሪያ ሆነ፡፡ በክርስቶስ ትንሣኤ ባገኘነው ክብር በትንሣኤ ዘጉባኤ እስክንነሣ ድረስ ብቻ ነፍስ ከሥጋ የሚለያዩበት ሆነ፡፡ “አሁንም ክርስቶስ ከሞቱ ሰዎች አስቀድሞ ተነስቷል።” እንዲል ሐዋርያው (፩ቆሮ.፲፭፥፳)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይበልጥ ሲያብራራውም “ሁሉ በአዳም እንደሚሞቱ እንዲሁ ሁሉ በክርስቶስ ደግሞ ሕያዋን ይሆናሉና። ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ተራ ይሆናል፤ ክርስቶስ እንደ በኩራት ነው፥ በኋላም በመምጣቱ ለክርስቶስ የሆኑት ናቸው ብሏል፡፡ (፩ቆሮ.፲፭፥፳፪-፳፫)፡፡ በመቀጠልም የሞትን በክርስቶስ ሞት ፍጹም መሻርና መደምሰስ ሲገልጽልን “የኋለኛው ጠላት ይሻራል፣ ይኸውም ሞት ነው” ሲል አስተምሯል፡፡ (፩ቆሮ. ፲፭፥፳፮)፡፡ በዚህም ሃይማኖቱን አጽንቶ፣ ምግባሩን አቅንቶ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምኖ የሚኖር ሰው ሁሉ ይህን ሞት የሚናፍቀው እንጂ የሚፈራውና የሚጠላው አይደለም፡፡
ለ. የቅዱሳን በገነት መክበር፣ የድል አድራጊዋ ቤተ ክርስቲያን ወይም የክርስቶስ መንግሥት መገለጥ
ጌታችን ከማረጉ በፊት ለሐዋርያት “በአባቴ ቤት ብዙ ማደሪያና ማረፊያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ኖሮ ቦታ ላዘጋጅላችሁ እሄዳለሁ እላችሁ ነበር፤ ከሄድሁና ቦታ ከአዘጋጀሁላችሁም ዳግመኛ እመጣለሁ፤ እናንተም እኔ ባለሁበት ትኖሩ ዘንድ ወደ እኔ እወስዳችኋለሁ” (ዮሐ.፲፬፥፪-፫) ብሏቸው ነበር፡፡ በጸለየ ጊዜም “አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር ስለ ወደድኸኝ የሰጠኸኝን ክብሬን እንዲያዩ እኔ ባለሁበት የሰጠኸኝ እነርሱ ደግሞ ከእኔ ጋር ይሆኑ ዘንድ እወዳለሁ” ማለቱም ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ (ዮሐ.፲፯፥፳፬)፡፡ በእርግጥ ሐዋርያቱም “ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና” (ፊል.፩፥፳፫) ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ እንደመሰከረው ከምድር ሕይወት ተለይተው ከእርሱ ጋር ለመሆን ይናፍቁ ነበር:: “በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘለዓለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ” እንዳላቸው ያውቃሉና፡፡ (፪ቆሮ. ፭፥፩)፡፡ እንዳለው ውጣ ውረድ፣ ድካም፣ ረኀብ፣ ጥም፣ ኃጢአት፣ ወዘተ ከአለበት ዓለም ይህ ሁሉ ችግር በሌለባት ዓለመ ነፍስ በሆነችው በገነት መኖር የተቻለው በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነው፡፡
በገነት ያለውን የቅዱሳን ሕይወት እንዴት እንደ ሆነ ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ገልጾታል፡፡ “በዙፋኑ ዙሪያም ሃያ አራት ዙፋኖች ነበሩ፥ በዙፋኖቹም ላይ ነጭ ልብስ ለብሰው በራሳቸውም የወርቅ አክሊል ደፍተው ሃያ አራት ሽማግሌዎች ተቀምጠው ነበር” (ራእ.፬፥፬)፡፡ “… ስለ እግዚአብሔር ቃልና ስለ ጠበቁት ምስክር የታረዱትን የሰዎች ነፍሳት ከመሠዊያ በታች” አየ፡፡ (ራእ.፮፥፱)፡፡ ከዚህ በኋላ በራእዩ ምን እንዳየ ሲነግረንም “…አንድ እንኳ ሊቆጥራቸው የማይችል ከሕዝብና ከነገድ ከወገንም ከቋንቋም ሁሉ እጅግ ብዙ ሰዎች ነበሩ፤ ነጭ ልብስም ለብሰው የዘንባባንም ዝንጣፊዎች በእጆቻቸው ይዘው በዙፋኑና በበጉ ፊት ቆሙ፤ በታላቅም ድምፅ እየጮሁ- በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው አሉ” ሲል ጽፎልናል፡፡ ከክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ በፊት ይህ ሁሉ አልነበረም፡፡ በእንዲህ ያለ ሕይወት መኖር የተቻለው ደግሞ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ የሞት ሥልጣን ከተሻረ በኋላ ነውና ይህን ክብር ለማግኘት ሁሉም ቅዱሳን ከዚህ ዓለም መሄድን ይመርጣሉ፡፡
በሰማይ ለቅዱሳን የተዘጋጁት ብርሃናማ መኖሪያዎች በቅዱሳት መጻሕፍት “የእግዚአብሔር ከተማ” (ዕብ.፲፪፥፳፪)፤ “የንጉሥ ከተማ”፤ “የጽዮን ተራራ” (መዝ.፵፯፥፪)፤ ፵፯፥፲፩)፤ “ሰማያዊት ኢየሩሳሌም”፣ (ቅድስት ማርያም)፣ “ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም” (ገላ.፬፥፳፮)፤ “አዲሲቱ ኢየሩሳሌም” (ራእ.፳፩፥፪) ተብለዋል፡፡ ስለዚህ ከትንሣኤው በኋላ በሰማይ ያለች የክርስቶስ መንግሥት ለቅዱሳን ተገለጠች፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩት ሁሉ ወደ ውስጧ ገቡ፡፡
እንደ ቅዱሳት መጻሕፍት አስተምህሮ፣ የቅዱሳን ሰዎች በገነት መክበር ስንል ፩ኛ. ከድካማቸው ማረፋቸውን፣ ፪ኛ. ከኀዘንና ከስቃይ እንግልት መለየታቸውን (ራእ.፲፬፥፲፫፤ ፥፲፮)፣ ፫ኛ. ከአበውና ከሌሎች ቅዱሳን ጋር ፍጹም የሆነ አንድነትን ማግኘታቸውን፣ ፬ኛ. እርስ በራሳቸውም ሆነ ከአዕላፍ መላእክት ጋር አንድ መሆናቸውን፣ ፭ኛ. ከበጉ ዙፋን ፊት ቆመው ማመስገናቸውንና እርሱን ማገልገላቸውን ነው፡፡
ሐ. ርደተ መንፈስ ቅዱስ
ጌታችን ከሕማማቱና ከስቅለቱ በፊት ለሐዋርያት ከእነርሱ ጋር እስከ ዘለዓለም ድረስ አብሮ የሚቆየውንና የሚያስተምራቸውን እንዲሁም እርሱ ያስተማራቸውን በማጽናት የሚመራቸውን ሌላኛውን አጽናኝ ከአብ የሚወጣ መንፈስ ቅዱስን እንደሚልክላቸው ቃል ገብቶላቸው ነበር፡፡ (ዮሐ.፲፭፥፳፮)፡፡ ከትንሣኤው በኋላም ለደቀ መዛሙርቱ ተገልጦላቸው የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ሲያድላቸው ይህንም ብሎ እፍ አለባቸውና መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ። “ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል አላቸው”፡፡ (ዮሐ.፳፥፳፪-፳፫)፡፡ ከዕርገቱ በዐሥረኛው ቀንም በበዓለ አምሳ መንፈስ ቅዱስን “እንደ እሳት በተከፋፈሉ ልሳኖች” ላከላቸው፡፡ (ሐዋ. ፪፥፫)፡፡
የመንፈስ ቅዱስ መውረድ በመጀመሪያ ለሐዋርያት በተሰጡት የመፈወስ፣ በልሣን የመናገርና በመሳሰሉት አስደናቂ ስጦታዎች የተገለጸ ሲሆን፣ በመቀጠልም በክርስቶስ የሚያምኑትን ሁሉ ወደ ፍጹምነትና ወደ ድኅነት በመውሰዱ የታወቀ፣ የተረዳ ሆኗል፡፡
“የመለኮቱ ኃይል፥ … ለሕይወትና እግዚአብሔርን ለመምሰል የሚሆነውን ነገር ሁሉ ሰጥቶናል፡፡ (፩ጴጥ. ፩፥፫)፡፡ እነዚህ የጸጋ ስጦታዎች ሁሉ ጌታችን በመሠረታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ይገኛሉ፡፡ የቅድስናችንንና የድኅነታችንን ምሥጢር ሁሉ የያዙ ናቸው፡፡
በአጠቃላይ ዋናው የክርስቶስ ሰው መሆን፣ መሰደድ፣ መራብ፣ መጠማት፣ መሰቀል፣ መነሣት በሰው ልጅ ላይ ሠልጥኖ የነበረውን ሞት ድል አድርጎ ሰውን ለማዳን ነው፡፡ እንደ ሰው ድንቅ ውለታ የተዋለለት ፍጥረት የለም፡፡ በአባቱ ሞት የዳነ፣ ጠላቱን ያሸነፈ፣ ሠልጥኖበት ከነበረው ጠላት ነጻ የወጣ የሰው ልጅ ብቻ ነው፡፡ በሰው ሰውኛው አንድ ሰው እናት አባት ሲሞትበት አሳዳጊ ያጣል፤ የሚያለብሰው፣ የሚያጎርሰው፣ የሚያስተምረው፣ ርስት ጉልቱን የሚያወርሰው እና ከድኅነት የሚያወጣው ያጣል፡፡ በአባታችን በክርስቶስ ሞት ግን ያጣነውን ሁሉ አግኝተናል፡፡ ባለጸጎች ሆነናል፤ ወደ ርስታችን ተመልሰናል፡፡ አሁንም በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምነን፣ የተከፈለልንን ውለታ እያሰብን በሃይማኖት ጸንተን እንድንኖር፣ እንዲሁ ከበዓለ ስቅለቱና ከበዓለ ትንሣኤው በረከት ያድለን ዘንድ አምላከ ቅዱሳን ፈቃዱ ይሁንልን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜ በጥቅምትና በግንቦት እንደምታካሂድ ይታወቃል፡፡ በዚህም መሠረት የግንቦቱ ርክበ ካህናት ትንሣኤ በዋለ ከ፳፭ኛው ቀን ጀምሮ ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም ከሰዓት በኋላ በጸሎት የተጀመረ ሲሆን ግንቦት ፲፰ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም በብፀዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የመክፈቻ ንግግር ተጀምሯል፡፡ እኛም ቅዱስነታቸው ያስተላለፉትን መልእክት ቀጥለን እናቀርባለን፡-

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

  • ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ፬ኛ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትየጵያ፣
  • ብፀዕ አቡነ ያሬድ፣
  • ብፀዕ አቡነ ዮሴፍ፣

የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፀዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፡-

የምሕረት አባት፣ የሰላም አለቃ የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን ለዓመታዊው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ስላደረሰን፣ በስሙ ልንወያይም ስላበቃን ክብርና ምስጋና ሁሉን ለሚችል ለኃያሉ አምላካችን ለእግዚአብሔር ይሁን፡፡

“ወተጸመዱ ለጸሎት ኵሎ ጊዜ በእንተ ኵሎሙ ቅዱሳን፡- ስለ ቅዱሳን ሁሉ ዘወትር ለጸሎት የተጠመዳችሁ ሁኑ” (ኤፌ.፮፥፲፰)

ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኘን የቤተ ክርስቲያናችንና የሃይማኖታችን ቁልፍ የግንኙነት መሣሪያ ጸሎት እንደሆነ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፡፡

እግዚአብሔር በሁሉ ያለና የሚገኝ ምሉእ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔር ሁሉንም ያውቃል፣ ያያልም፣ ነገሮች ከመሆናቸው ወይም ከመታሰባቸው በፊት ሳይቀር ድንበርና ወሰን በሌለው ዕውቀቱ ያውቃል፡፡ ይሁንና ቢያውቅም ለፍጡራን ሁሉ በተለይም አእምሮና ለብዎ ላላቸው መላእክትና ሰዎች የተሰጣቸውን ብሩህ አእምሮ ተጠቅመው የሚበጃቸውን በራሳቸው እንዲመርጡና እንዲወስኑ ፍጹም ነፃነትን አጎናጽፏቸዋል፡፡

ሰዎችም ሆኑ መላእክት ይህንን ነፃነት ተጠቅመው ያለ ምንም ተፅዕኖ ሲወስኑ በውሳኔአቸው ላይ እግዚአብሔር ተፅዕኖ አያደርግም፡፡

ውሳኔአቸውን ተከትሎ በሚመጣው ውጤት ግን ይጠይቃል፣ ዳኝነትም ይሰጣል፡፡ የመላእክትም ሆነ የሰዎች ውድቀት ሊከሰት የቻለው በዚህ ነፃ ምርጫና ውሳኔ እንደሆነ ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረን እውነት ነው፡፡ ዛሬም በዓለም እየሆነ ያለው ይኸው እውነት ነው፡፡

ሰው የከፋ ኃጠአትን ለመፈጸም ሲሮጥ ምክርና ትምህርት ከመስጠት ባለፈ እግዚአብሔር በነገሩ ጣልቃ ገብቶ ሲያስቆም አናይም፡፡

“አቅረብኩ ለከ እሳተ ወማየ፣ ደይ እዴከ ኀበ ዘፈቃድከ፡- እሳትንና ውኃ አቅርቤልሃለሁ፤ እጅህን ወደፈለግኸው ክተት” የሚለውም ይህንን እውነታ ያመለክታል፡፡

ከዚህ አንጻር ሰው መከራዎችንና ፈተናዎችን እየሳበና እየጎተተ የሚያመጣቸው በራሱ ነፃ ምርጫና ውሳኔ እንጂ በሌላ ተጽእኖ እንዳይደለ እናስተውላለን፡፡

የርኩሳን መናፍስት ተፀዕኖ እንዳለ የምናይበት ጊዜ ቢኖር እንኳ መግቢያቸው የሰው ነፃ ዝንባሌ እንደሆነ በአዳምን ሔዋን ያየነው እውነት ነው፡፡

ከዚህ ሌላ ደግሞ ሰዎች በሌሎች ምክንያቶች ሲፈተኑና መከራ ላይ ሲወድቁ የምናየው እውነት ነው፤ ከዚህም አኳያ በቃየን ምክንያት አቤል ሕይወቱን ሲያጣ እንመለከታለን፡፡ ስለዚህ ሰዎች በኃጢአት ምክንያት ከወደቁ በኋላ በራሳቸው ምርጫና ውሳኔ ወይም በሌላ ወገን ግፊት ፈተና ላይ ሲወድቁ እናያለን፡፡

  • ብፀዕ ወቅዱስ አባታችን፣
  • ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፤

የምንኖርባት ዓለመ ሰብእ ከላይ በተጠቀሱት ምክንያቶች ምን ጊዜም ከመከራን ከፈተና ተለይታ አታውቅም፡፡ ይህ የማይቀር ነገር መሆኑን የሚያውቅ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠን መርሕ ቢኖር፡- “ትግሁ ወጸልዩ ከመ ኢትባኡ ውስተ መንሱት፡- ማለትም ወደ ፈተና እንእንዳትገቡ ትግታችሁ ጸልዩ” የሚለው ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ጌታችንን ተከትሎ ዘወትር ስለ ቅዱሳን እንድንጸልይ አስተምሮናል፡፡

ከዚህ አንጻር ከመከራና ከፈተና ለመዳን የተሰጠን የመዳኛ ስልት ተግቶ መጸለይ ነው፤ ስንጸልይም ለራሳችን ብቻ ሳይሆን ለቅዱሳን ሁሉ ተግተን ዘወትር መጸለይ እንዳለብን ተነግሮናል፤ ኃላፊነትም አለብን፡፡

ቤተ ክርስቲያን በደመ ክርስቶስ አንጽታ ስለቀደሰቻቸው ምእመናን ልጆቿ ዘወትር ስትጸልይ የምትኖረውም ከዚህ የተነሣ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን ስለሆኑ ምእመናን ብቻ ሳይሆን ስለ ዓለሙ ሁሉ ማለትም ስለ ሰማዩ፣ ስለ ምድሩም፣ ስለ እንስሳቱም በአጠቃላይ ስለ ፍጥረት ሁሉ ትጸልያለች፡፡ ይሁንና በአሁኑ ጊዜ ደግሞ በሀገራችን፣ በሕዝባችንና በደመ ክርስቶስ በተቀደሱ ክርስቲያን ልጆቻችን ላይ ከበድ ያለ ፈተና እየተከሰተ ስለሆነ ከምን ጊዜም በላይ ወደ እግዚአብሔር አጥብቀን ልንጸልይ፣ ልናለቅስና ልናዝን ይገባናል፡፡

ገዳማትና አድባራት፣ መነኮሳትና ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና ወጣቶች፣ ምእመናንና ምእመናት ፈተና ላይ ሲወድቁና መከራ ሲጸናባቸው ቅዱስ ሲኖዶስን በቀጥታ የሚመለከተው ስለሆነ የመፍትሔው አካል ሆኖ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡

ይህንን የፈተና ጊዜ አይተን እንዳላየን፣ ሰምተን እንዳልሰማን በዝምታ የምናልፈው ከሆነ ለቤተ ክርስቲያናችን ጠባሳ ታሪክ መሆኑ አይቀርም፤ በእግዚአብሔርም ተጠያቂነትን ማስከተሉ አይቀርም፡፡ ምእመናን ልጆቻችንም በዚህ ጉባኤ ላይ አመኔታ እንዳያጠ በጣም መጠንቀቅ አለብን፡፡

ይህ ጉባኤ በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች እየተጎዱ ለሚገኙት ምእመናንና ምእመናት እንደዚሁም በአጠቃላይ ያለ ፍትሕ እየተጎዱ ለሚገኙ ሰዎች መፍትሔ አምጪ አካል ሆኖ ከጎናቸው ሊቆም ይገባል፡፡ ይህንንም ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በተሰጠው የጥበቃ ኃላፊነት መሠረት በጸሎት፣ በማስታረቅ፣ በቁሳቁስ ማለትም መጠለያ፣ ምግብ፣ መጠጥ፣ ልብስና መድኃኒት በማቅረብ ሊያከናውነው ይገባል፡፡ ይህ መሰሉ ቅዱስ ተግባር ለቤተ ክርስቲያናችን አዲስ ነገር ሳይሆን ስታደርገው የነበረና አሁንም እያደረገችው የሚገኝ ነው፡፡ የአሁኑ ከሌላው ጊዜ ልዩ የሚያደርገው ነገር ቢኖር የችግሩ ክብደትና ውስብስብነት ማየሉ ነው፡፡

ይሁን እንጂ ሕልም አለ ተብሎ መተኛት እንደማይቀር ሁሉ ክብደቱን አይተን የምንሸሸው ሳይሆን የቤተ ክርስቲያናችን የውስጥ ዓቅምን በማየት የምእመናንን ትብብርና እገዛ በመጠየቅ፣ እንደዚሁም የዓለም አብያተ ክርስቲያናትና ልዩ ልዩ በጎ አድራጊዎችን በማስተባበር መከራውንና ፈተናውን መቋቋም ይኖርብናል፤ ለዚህም የዛሬ ሠላሳ ዓመት ገደማ የነበረው ዓይነት አሠራር ዘርግተን ብንሠራ ሰውን ከረሃብ እልቂት ማዳን እንችላለን፡፡

ስለሆነም ቅዱስ ሲኖዶስ በዚህ ዙሪያ በሰፊው መክሮበት ውሳኔ እንዲያሳልፍ በዚህ የመክፈቻ ጉባኤ በአጽንዖት እናሳስባለን፡፡

በመጨረሻም፡-

ለመንግሥትም ሆነ ለሁሉም ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ እንደዚሁም ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ማስተላለፍ የምንፈልገው የአደራ መልእክት ቢኖር፣ የሁሉም ነገር መሠረትና የችግሮቻችን ሁሉ መፍትሔ ሰላምና ሰላም ብቻ መሆኑን በመገንዘብ ለሰላም ሲባል አስፈላጊ የሆነ ዋጋ መክፍል እጅግ አስፈላጊ መሆኑ ነው፡፡ ዋስትና ያለው ሰላም በሀገራችን ሊረጋገጥ የሚችለው ደግሞ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በጠረጴዛ ዙሪያ ተሰባስበው መወያየት፣ መግባባትና ሀገራዊ ስምምነት መፈጸም ሲችሉ ነው፡፡

ስለሆነም ይህ ለነገ የማይባል፣ የህልውናችን ጥያቄ መልስ መሆኑን አውቀን ሁላችንም በዚህ መልካም ሥራ እንድንተባበር በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላለፋለን፡፡

እግዚአብሔር የተባረከ የተቀደሰ ጉባኤ ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፲፰ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም

አዲስ አበባ

ኢትዮጵያ

“ፋሲካችን ክርስቶስ ተሠውቶ የለምን?”( ፩ኛቆሮ.፭፥፯)

በቀሲስ ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

ፋሲካ ማለት ማለፍ፣ መሻገር፣ ደስታ  ሲሆን በዕብራይስጥ  “ፓሳሕ” ይለዋል፡፡ ይህም ዐለፈ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም በትንሣኤ በዓል የሚዘመረውን የመዝሙር ክፍል “ፋሲካ” በማለት ሰይሞታል፡፡ ይኸውም “ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ ተሐፂባ በደመ ክርስቶስ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካን ታደርጋለች” በማለት እንደተናገረው እኛም እርሱን አብነት አድርገን በእርሱ ዜማ እያመሰገንን ትንሣኤውን እየመሰከርን በትንሣኤውም ያገኘነውን ትንሣኤ ዘለ ክብር(የክብር ትንሣኤ) እያሰብን እናከብራለን፡፡

የፋሲካ በዓል የሚከበረው የክርስትና እምነት ተከታዮች ሁሉ ባሉበት በኅብረት ወይም በጋራ ነው፡፡ ምክንያቱም በዓሉ የሁሉ ነውና፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ እንደጠቀሰው “የክርስቶስ ፍቅር በዚህ ሐሳብ እንድንጸና ያስገድደናል ሁሉ ፈጽመው ስለ ሞቱ  አንዱ ስለ ሁሉ ቤዛ ሆኖ ሞቶአልና በሕወት የሚኖሩትም ስለ እነርሱ ቤዛ ሆኖ ለሞተውና ለተነሣውም እንጂ ወደፊት ለራሳቸው የሚኖሩ እንዳይሆኑ እርሱ ስለ ሁሉ ቤዛ ሆኖ ሞተ” (፪ኛቆሮ.፭፥፲፬) በማለት የብዙኀን በዓል መሆኑን ያስረዳል፡፡

ለአማናዊው ፋሲካችን ምሳሌ የነበረው ኦሪታዊው የፋሲካ በዓል አከባበር የሚጀምረው የእስራኤል ከግብጽ መውጣት ጋር ተያይዞ ነው፡፡ የእስራኤል ልጆች በግብጽ ሀገር ሲኖሩ መከራው ቢጸናባቸው የእግዚአብሔርን ክንድ ደጅ መጥናታቸውን ተከትሎ ከግብጽ እንዲወጡ ሙሴን መሪ(መስፍን)፣ አሮንን አፍ (ካህን) አድርጎ እግዚአብሔር ቢያዛቸውም ፈርዖን እግዚአብሔርን አላውቅም እስራኤልንም አለቅም በማለቱ በዘጠኝ መቅሠፍት ግብፃውያን ተመተው እግዚአብሔርን መስማት እስራኤልንም መልቀቅ ስላልፈቀዱ በዐሥረኛ  ሞተ በኵር ተቀጡ፡፡

መቅሠፍቱ በእግዚአብሔር ላይ ያመፀውን ፈርዖንንና ግብጻውያንን የሚቀጣ በመሆኑ የእስራኤል ልጆች መቅሰፍቱ እንዳያገኛቸው ብሎም ለእግዚአብሔር የተለዩ መሆናቸው እንዲታወቅ ለሙሴ በተነገረው መሠረት በየወገናቸው የአንድ ዓመት ጠቦት  አርደው  ደሙን በቤታቸው በሁለቱ መቃኖችና በጉበኑ ላይ በመርጨት ምልክት አደረጉ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ   ያንን የደም ምልክት እያየ የእስራኤልን ልጆች እያለፈ የግብጻውያንን በኵር ሁሉ  በሞት ቀጣቸው፡፡ ያ ስለ እስራኤላውያን ደኅንነት የታረደ በግ በደሙ ምልክት አማካይነት የእስራኤን ልጆች ከግብጻውያን ጋር በሞት ከመቀጣት ያመለጡበት ሥርዓት ነው፡፡ የእስራኤል ልጆች ከግብጽ ባርነት ተላቀው ከፈርዖን እጅ አምልጠው ወደ ተስፋዪቱ ምድር ለመግባት ጉዞ ለመጀመራቸው ሳይወድ በግድ የፈርዖንን እሺታ ያስገኘ ዐሥረኛው መቅሠፍት ሞተ በኵር ነው፡፡

ለፋሲካ የሚታረደውም በግ ፋሲካ ይባል ነበር (ዘፀ.፲፪፥፩-፲፫)፡፡በግብጻውያን ቤት ልቅሶ ሲሰማ በእስራኤላውያን ቤት ከበጉ ደም የተነሣ መጠበቅ (የቀሳፊው ሞት ማለፍ) ሆኖላቸው ደስታ የተሰማበት፣ የእግዚአብሔር ትድግና የታየበት ስለሆነ ፋሲካ ተባለ፡፡፡

የእስራኤል ልጆች ከእግዚአብሔር  በታዘዙት መሠረት በመጀመሪያ ወራቸው በዐሥራ አራተኛው ቀን የፋሲካን በዓል ያከብራሉ፡፡ ከዚያም ምሽት እስከ አንድ ሳምንት ድረስ የቦካውን ነገር ለመብላት ስላልተፈቀደላቸው ሙሉ ሳምንቱ የቂጣ በዓል ተባለ፡፡ እስራኤል ከግብጽ ሲወጡ በችኮላ ስለነበር ያልቦካ ቂጣ መብላታቸውን የሚያስቡበት ነው፡፡ እስራኤል ከግብጽ ወጥተው ወደ ተስፋዪቱ ምድር መግባታቸው የሰው ልጅ ከሲዖል ወደ ገነት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከመገዛት ወደ ነጻነት፣ ከባርነት ወደ ልጅነት ለመግባታችን(ለመሻገራችን) ምሳሌ ነው፡፡

የእስራኤል ልጆች በታረደው በግ ደም አማካኝነት ከሞት ማምለጣቸው በአማናዊው በግ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከዲያብሎስ ቁራኝነት ከሲዖል ባርነት ተላቀን ሞታችን በሞቱ ተወግዶልን ሕይወትን የማግኘታችን ምሳሌ ነው፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ  የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን በመከረበት ትምህርቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ፋሲካችን” እያለ ሲገልጸው የምናየው፡፡

“እንግዲያስ መታበያችሁ መልካም አይደለም ጥቂቱ እርሾ ብዙውን ሊጥ እንደሚያመጥ አታውቁምን እንግዲህ ለአዲስ ቡሆ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ ከእናንተ አርቁ፤ ገና ቂጣ ናችሁና ፋሲካችን ክርስቶስ ተሠውቶ የለምን? አሁንም በዓላችሁን አድርጉ ነገር ግን እውነትና ንጽሕና ባለው እርሾ ነው እንጂ በአሮጌው እርሾ በኃጢአትና በክፋት እርሾም አይደለም”(፩ኛ ቆሮ.፭፥፮) በማለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ፋሲካችን ይለዋል፡፡

በመከራው መከራችንን አስወግዶ፣ በሞቱ ሞታችንን ሽሮ፣ በትንሣኤው ትንሣኤያችንን አውጆልናልና ፋሲካችን ክርስቶስ ነው፡፡ ለዚህም ነው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ድጓ በተሰኘው ድርሰቱ በዕለቱ ማለትም በበዓለ ፋሲካ (በትንሣኤ ዕለት) በሚቆመው የመዝሙር ክፍል “ይትፌሣሕ ሰማይ ወትትሐሠይ ምድር…፣ ሰማይ ይደሰታል፣ ምድርም ሐሤት ታደርጋለች” ይልና ዝቅ ብሎ “ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ ተሐፂባ በደመ ክርስቶስ፣ ምድር በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካን አደረገች” በማለት ያመሰገነው፡፡

በዓለ ፋሲካ አንዱ ክርስቶስ ስለ ሁሉ የሞተበት፣ ሕዝብና አሕዛብ አንድ የሆኑበት ሰማያውያንና ምድራውያን የተደሰቱበት፣ የራቁት የቀረቡበት፣ የአዳም ተስፋ የተፈጸመበት ታላቅ በዓል ነው፡፡ በዚህ በዓል የተጣላ ታርቆ፣ የበደለ ክሶ፣ የተበደለ ይቅር ብሎ እግዚአብሔር ለሰው ያደረገውን በአንድያ ልጁ ቤዛነት ያሳየንን ፍጹም ፍቅሩን እያደነቅን እርስ በእርሳችን በፍቅር ተሳስረን ያለን  ለሌላቸው አካፍለን፣ ድሃ ሀብታም ሳንል፣ ብሔር፣ ቋንቋ፣ ፆታ  ሳንለይ  ሁላችን  የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ  ልጆች  መሆናችንን ላፍታም ሳንዘነጋ መሆን አለበት፡፡

በዓለ ፋሲካ ወይም በዓለ ትንሣኤ ከመጀመሪያው የትንሣኤ ቀን አንሥቶ እስከ በዓለ ኀምሳ ማለትም እስከ ኀምሳኛው ቀን ድረስ ትንሣኤ ሕይወትን እያሰብን ደስ ብሎን የምናከብረው የደስታ በዓላችን ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ትንሣኤ የሚታሰበው በዚህ ቀን ብቻ ነው ማለት ሳይሆን በልዩ የአምልኮ ሥርዓት ትንሣኤ ክርስቶስን እያሰብን እኛም እንዲሁ ትንሣኤ ዘለ ክብር እንዳገኘን በምልዓት የምንመሰክርበት ወቅት በመሆኑ ነው፡፡ ደስታችንም ከወገኖቻችን ጋር ባለን ነገር እየተሳሰብን መሆን ይኖርበታል፡፡ ምክንያቱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዓለሙ ሁሉ ድኅነት በመስቀል ላይ ዋለ እንጂ ለአንድ ጎሳ ወይም ለአንድ ሀገር ወይም ለአንድ ቋንቋ ተናጋሪ አይደለም፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደ ጻፈው “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ሕወት እንዲያገኝ እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ቤዛ አድርጎ እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲህ   ወዶታልና” ይላል፡፡(ዮሐ.፫፥፲፮)፡፡ በዚህ ገጸ ንባብ ላይ ዓለም የተባለ ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ሰውን የወደደውና የባህርይ ልጁን ቤዛ አድርጎ እስከ መስጠት ያደረሰው ፍቅር ነው፡፡ የክርስትና ሃማኖት የተመሠረተውም በፍቅር ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን በሚኖርበት አካባቢም ሆነ  በተገኘበት ቦታ ሁሉ በወንድሞቹ መካከል በፍቅር ሊመላለስ ይገባዋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ “ወንድሞቻችን ሆይ እንግዲህ ደስ ይበላችሁ ጽኑ ታገሡ በአንድ ልብም ሁኑ በሰላም ኑሩ፤ የሰላምና የፍቅር አምላክም ከእናንተ ጋር ይሁን በተቀደሰ ሰላምታ እርስ በርሳችሁ ሰላም ተባባሉ” (፪ኛቆሮ.፲፫፥፲፩) በማለት እንዳስተማረን ሆነን ልንኖር ተጠርተናል፡፡  ሞትን በሞቱ ሽሮ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ በኃይልና በሥልጣን የተነሣውን አምላካችንን  እንደ ቅዱስ ያሬድ በዝማሬ ስናመሰግነውም “ትንሣኤከ ለእለ አመነ ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ፤ ለእኛ ትንሣኤህን ለምናምን ብርሃንህን በላያችን ላክልን” በማለት የትንሣኤውን ብርሃን እንዲልክልን ስንለምነው ያደፈ ማንነታችን መቀደስ የመጀመሪያ ሥራችን አድርገን ነው፡፡

እግዚአብሔር ንጹሓ ባሕርይ ነውና በንጹሕ ሰውነታችን ላይ ስለሚያድር ከወደቅንበት ኃጢአት በንስሓ ዕንባ ታጥበን መነሣት እና ቤተ መቅደስ ሰውነታችን ንጹሕ ማድረግ ይኖርብናል፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ማደሪያዎች ለመሆን ዳግም በክርስቶስ ተሠርተናልና እርሱን የጽድቅ ልብሳችን አድርገነዋል፡፡ በእርሱ ልብስነት የተሸፈነ /ያጌጠ/ ማንነታችን ደግሞ ለሁሉ ፍቅርን የሚያደርግ ይሆናል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ክርስቲያኖች በላከላቸው መልእክቱ “እንግዲህ የጨለማን ሥራ ከእኛ እናርቅ፣ የብርሃንንም ጋሻ ጦር እንልበስ በቀን እንደሚሆን በጽድቅ ሥራ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር፣ በዝሙትና በመዳራትም አይሁን በክርክርና በቅናትም አይሁን ነገር ግን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት የሥጋችሁንም ምኞት አታስቡ”  እንዲል፡፡(ሮሜ ፲፫፥፲፪)

ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን በዓለ ትንሣኤውን ስናከብር የጨለማን ሥራዎች ከእኛ ማራቅ ይጠበቅብናል፡፡ እነርሱም ትዕቢት፣ አመጽ፣ ክፋት፣ ስግብግብነት፣ ፍቅረ ንዋይ፣ ዘረኝነት፣ ቁጣ፣ ቅንዓት፣ ዝሙት፣ ነፍሰ ገዳይነት፣ ሐሜት፣ ዘፋኝነት ወዘተ ሲሆኑ እነዚህን ክፉ ሥራዎች ከእኛ በማራቅና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያሳየንን ፍጹም ፍቅር ተገንዝበን እርሱን ልንለብስ ይገባናል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት ካለ በኋላ በሌላው ክፍል ደግሞ “እንግዲህ እግዚአብሔር እንደመረጣቸው ቅዱሳንና ወዳጆች ምሕረትንና ርኅራኄን፣ ቸርነትንና ትሕትናን፣ የውሀትንና ትዕግሥትን ልበሱት ባልንጀሮቻችሁን ታገሡአቸው እርስ በእርሳችሁ ይቅር ተባባሉ፤ ባልንጀሮቻችሁን የነቀፋችሁበትን ሥራ ተዉ፣ ክርስቶስ ይቅር እንዳላችሁ እናንተም እንዲሁ አድርጉ፤ ከዚህም ሁሉ ጋር ዘወትር ተፋቀሩ የመጨረሻው ማሠሪያ እርሱ ነውና” በማለት እንደመከረን መንፈሳዊ ፍሬ የምናፈራ መሆን እንዳለብን  ይመክረናል፡፡(ቆላ.፫፥፲፪)

እንግዲህ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መራራውን ሞት የተጎነጨ፣ ሕማማተ መስቀሉን በፍቅር የተቀበለ እኛን ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከባርነት ወደ ነፃነት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ለመመለስ እርሱ ሁሉን ፈጽሞ ስለ እኛ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቷልና፡፡ በከበረ  ደሙ ፈሳሽነት ከኃጢታችን ሁሉ ነጽተናል፡፡ ስለሆነም ንጽሕናን ቅድስናን እንደ ልብስ ተጎናጽፈን እንድንኖር አዲሱን ልብስ ክርስቶስን እንልበስ፡፡

የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር የትንሣኤውን ብርሃን ለሁላችን ያድለን አሜን፡፡

የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ

ክፍል አንድ

መ/ር ሕሊና በለጠ

የክርስቶስ ሞቶ መነሣት ለትንሣኤያችን መጀመሪያ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሞቱና በትንሣኤው ትንሣኤያችንን ባያረጋግጥልን ኖሮ ሃይማኖት ዋጋ አያሰጥም ነበር፡፡ የአማኞችም ሕይወታቸው በክርስቶስ ሞትና በትንሣኤው በተገኘ ሕይወት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ለዚህም ነው የጥንት ክርስቲያኖች “ማራናታ” እያሉ ሰላምታ ይለዋወጡ የነበሩት፡፡ “ማራናታ” ማለት “ክርስቶስ የተነሣው፣ ያረገውና ዳግም የሚመጣው” ማለት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችንም ይህ ትውፊት ቀጥሎ በሰሙነ ትንሣኤና በበዓለ ሃምሳ “ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን፣ በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን…፤ክርስቶስ በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ከሙታን ተለይጦ ተነሣ” እያልን ሰላምታ እንለዋወጣለን፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የክርስቶስ ትንሣኤ ለክርስትና መኖርና በክርስትናችን ጸንተን ለምናገኘው ትንሣኤ የግድ አስፈላጊ እንደ ነበር “ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷል ብለን ለሌላው የምናስተምር ከሆነ እንግዲህ ከመካከላችሁ ሙታን አይነሡም የሚሉ እንዴት ይኖራሉ? ሙታን የማይነሱ ከሆነ  ክርስቶስም ከሙታን ተለይቶ አልተነሣማ፤ ክርስቶስም ካልተነሣ እንግዲያስ ትምህርታችን ከንቱ ነው፤ የእናንተም እምነታችሁ ከንቱ ነው፤ …በዚህ ዓለም ሕይወት ብቻ ክርስቶስን ተስፋ ከአደረግነው፥ ከሰው ሁሉ ይልቅ ጉዳተኖች ነን” (፩ቆሮ.፲፭፥፲፪-፲፱)፡፡ በማለት በአጽንዖት አስተምሯል፡፡

በመስቀል ላይ ሞቶ ሞትን ድል መንሣቱ

“እግዚአብሔር ወልድ ለምን ሰው ሆነ?” የሚለውን ጥያቄ ሲመልሱ ቅዱሳን አበው “ወልደ እግዚአብሔር ሰው የሆነው ለሰው ሁሉ ሕይወትን ለመስጠት ነው” ይላሉ፡፡ እግዚአብሔር ብቻውን ሕያው ነው፡፡ “እርሱ ብቻ የማይሞት ነው” (፩ጢሞ.፮፥፲፮)፡፡ ስለዚህ መዋቲ የሆነው ሰው ጽድቅንና ሕይወትን የሚያገኘው በጸጋ ነው፡፡ “ያዳነን በቅዱስ አጠራሩም የጠራን እርሱ ነውና፤ ዓለም ሳይፈጠር በኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰጠን እንደ ፈቃዱና እንደ ጸጋው እንጂ እንደ ሥራችንም አይደለም፤ ይህም ሞትን በሻረው ሕይወትንም በገለጣት በወንጌሉም ትምህርት ጥፋትን ባራቀ በጌታችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት ዛሬ ተገለጠ።” (፪ጢሞ. ፩፥፱-፲) በማለት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለደቀ መዝሙሩ ጢሞቴዎስ በጻፈው መልእክቱ እንደገለጠለት የእርሱን ዘለዓለማዊነት (ሕያውነት) በጸጋ አድሎ የፈጠረው የሰው ልጅ የተሰጠውን ሀብት በማጣቱ፣ ያጣውን ሀብት ይመልስለት ዘንድ አምላክ ሰው ሆነ በመስቀልም መከራ መስቀልን ተቀበለ፡፡

ሞተን የነበርን እኛ ሕይወትን አግኝተን የማንሞት እንሆን ዘንድ ሞት ራሱ መሞት አለበት፡፡ ይህ ይሆን ዘንድ በመለኮቱ የማይሞት እግዚአብሔር ወልድ በሥጋ ሞተና ሞትን ድል አደረገ፡፡ ይህንን ቅዱስ ጳውሎስ ሲገልጽልን “ይህ የሚፈርሰው የማይፈርሰውን በለበሰ ጊዜ፣ የሚሞተውም የማሞተውን በለበሰ ጊዜ፣ “ሞት በመሸነፍ ተዋጠ” ተብሎ የተጻፈው ያን ጊዜ ይፈጸማል፡፡ ሞት ሆይ እንግዲህ መውጊያህ ወዴት አለ? መቃብር ሆይ አሸናፊነትህ ወዴት አለ? የሞት መውጊያ ኃጢአት ናት፣ የኃጢአትም ኃይልዋ ኦሪት ናት፡፡” (፩ቆሮ.፲፭፥፶፬-፶፮) በማለት ሞት በመስቀለ ክርስቶስ ድል መነሳቱን ገልጾልናል፡፡ ከዚያም ሞት በመስቀለ ክርስቶስ ድል በመሆኑ አዲስ ሕይወትን በትንሣኤው አገኘን፡፡ “በኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ አዲስ ፍጥረት መሆን ነው እንጂ መገዘር አይጠቅምም፣ አለመገዘርም ግዳጅ አይፈጽምም” እንዲል (ገላ.፮፥፲፭)፡፡

በሌላ አገላለጽ “አሮጌው ሰውነታችን” በሞትና በኃጢአት ከእግዚአብሔር የተለየ ሆነ፡፡ አዳም ሲበድል የሰብእና ባሕርዪ በሞላ በሞት ተበከለ፡፡ የመጀመሪያዎቹ ወላጆቻችን የእግዚአብሔር ሕግና ትእዛዝ በመተላለፍ እነርሱንም ሆነ ልጆቻቸውን ለሞት አሳልፈው ሰጡ፡፡ በመሆኑም ሁላችን ሞተን ነበር፤ ኃጢአትን በመፈጸምም የምንሞት ሆንን፡፡ “የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነውና፤ የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን የዘለዓለም ሕይወት ነው” እንዲል፡፡(ሮሜ.፮፥፳፫)፡፡

ስለዚህ ለዚህ ጥፋት ዋናው መፍትሔ ሞትን ማጥፋት ነበር፡፡ ሞትን ማጥፋት ደግሞ ለፍጥረታት የሚቻል አይደለም፡፡ ቅዱስ አቡሊዲስ ዘሮም “ሙሴም ሞትን ያጠፋ ዘንድ አልቻለም፤ እርሱንም ይዞ ገዛው እንጂ፡፡ ከእርሱም በኋላ የተነሡ ነቢያትንም ሁሉ ሞት ገዛቸው እንጂ፡፡ ክርስቶስ ግን በቸርነቱ ለሁሉ ሕይወትን ሰጠ” ብሏል፡፡ ሞት ከጠፋ፣ ሰው የማይሞት ከመሆኑም ባለፈ የሞት መንገድ ከሆነው ከኃጢአትም ነጻ መውጣት ይችላል፡፡ በክርስቶስ ሕያው የሆነ ሰው ኃጢአትን አይሠራም፤ በሥጋ ቢሞትም ፈርሶ በስብሶ አይቀርም፤  በትንሣኤ ዘጉባኤ ይነሣል፡፡ ሰው የማይሞት ከሆነ ከእግዚአብሔር ባሕርይ በጸጋ ለመሳተፍ (ሱታፌ አምላክ) የሚቻለው ይሆናል፡፡ በመሆኑም በሞቱ ሞትን ለማጥፋት “የሰውን ልጅ ሊያገለግል፣ ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ” በፈቃዱ ወደ መስቀሉ ሔደ፡፡ (ማቴ.፳፥፳፰፤ማር.፲፥፵፭)፡፡ እንዲል በበደሉ ምክንያት ስለጠፋው የሰው ልጅ ሲል የማይሞተው ሞተ፤ በዓለም ላይ ሠልጥኖ የነበረውንም ባለሥልጣን ሻረ፤ ነጻነቱን አጥቶ በጽኑ ግዞት የነበረው የሰው ልጅ የአጣውን ነጻነት ተጎናጸፈ፡፡

ከኃጢአት ብቻ በቀር እንደኛ ሰው ሆኗልና ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በፈቃዱ ለየ፣ ማለት በሥጋ ሞተ፤ ከሙታንም ተለይቶ ተነሣ፡፡ በእውነትም መለኮት በሥጋ ሞቶ ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፡፡ “ምትሐት ያይደለ በእውነት ተራበ፣ ተጠማ እንጂ፡፡ ዳግመኛም ከኃጥአን ከመጸብሓን ጋር በላ፣ ጠጣ፤ ራሱን አሳልፎ ለመስቀል ሰጠ፤ እጁን እግሩን ተቸነከረ፤ ጎኑን በጦር ተወጋ፤ ከእርሱም ቅዱስ ምሥጢር የተገለጠበት ደምና ውኃ ፈሰሰ /ወጣ/” በማለት ታላቁ ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ ተናገረ፡፡ የእኛን በደል ሳይሠራ በእኛ ላይ ሊደርስ የሚገባውን ሁሉ ተቀበለ፡፡

ይህ ሁሉ መከራ የደረሰበት ግን ሥጋን ተዋሕዶ ነው፡፡ በመለኮቱ እንዲህ ሆነ እንዳንል አበው ያስጠነቅቃሉ፡፡ ታላቁ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ይህንን ሲያስተምር “እጆቹን፣ እግሮቹን በተቸነከረባቸው ችንካሮች መወጋቱንም እናምናለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ እርሱ ደዌያችንን ወሰደ ሕማማችንንም ተሸከመ፤ እኛን ለማዳን ኃጢአታችንንም ይቅር ለማለት መከራ ተቀበለ እንዳለ፡ በባሕርዩ ሕማም የሌለበት ሲሆን በሥጋ የታመመ ነው፤ በእርሱ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ድነናል አለ፡፡ መለኮት ሥጋን ተዋሕዶ በተገረፈና በተቸነከረም ጊዜ በመከራው ሁሉ መለኮትን ሕማም ተሰማው የሚል ሰው ቢኖር የተለየ የተወገዘ ይሁን” ብሎ ገልጧል፡፡ አምላክ በባሕርዩ የማይራብ፣የማይጠማ፣ የማይደክም፣የማይታመም፣ የማይሞት ነው፡፡ ነገር ግን  በሥጋ ተራበ፤ ተጠማ፤ ተሰደደ፤ ደከመ፤ ታመመ፤ ሞተ፡፡ በዚህም አስተምህሮ ጸንቶ መኖር ያስፈልጋል፡፡

ይህ ማለት ግን መለኮቱን ከትስብእቱ መለየት እንዳልሆነ ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ቅዱስ አዮክንድዮስ ዘሮም “በመስቀል በሥጋ ተሰቅሎ ሳለ ለመለኮት ከሥጋ መለየት የለበትም፡፡ አንዲት ሰዓትም ቢሆን የዐይን ጥቅሻ ያህል ስንኳ ቢሆንም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፤ በመቃብር ውስጥ ሳለም መለኮት ከትስብእት አልተለየም” ያለው ይህንን በደንብ እንገነዘብ ዘንድ ነው፡፡

ቅዱስ ዲዮናስዮስ ዘአንጾኪያ ይህንንም በጥንቃቄ ሲያስረዳ “እርሱ መቼም መች ከመለኮቱ ሳይለይ የሰውነትን ሥራ ሁሉ ገንዘቡ አደረገ፡፡ ይኸውም መራብ፣ መጠማት፣ መንገድ በመሔድ መድከም፣ በመስቀል ላይ መሰቀል፤ በብረት ችንካር መቸንከር ነው፡፡ በሰውነቱ መቼም መች ሰው ነው፤ በአምላክነቱ ሰውን የፈጠረ ነው፤ ግን ከማይከፈል ተዋሕዶ በኋላ መከፈል የለበትም፡፡ ሰው እንደ መሆኑ ስለ እኛ የታመመውና የሞተው እርሱ ነው፡፡ በመለኮቱ ግን መቼም መች አይታመምም፤ አይሞትም፤ ሕማምንና ሞትንም አይቀበልም፡፡ በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፡፡ ሲኦልንም የበዘበዘው እርሱ ነው” ብሏል፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው ማለትም በሥጋ የታመመ፣ የሞተ፣ ነፍሱም ከሥጋው በተለየ ጊዜ ሥጋውን ገንዘው የቀበሩት እኛን ከሲኦል ለማዳን ወደ ጥንተ ክብራችን ልጅነት፣ ወደ ጥንተ ቦታችን ገነት ለማስገባት እንደሆነ ልብ ልንል ይገባል፡፡

ነገር ግን ስለ ድል መንሣቱ ሌላ የምንናገረውም ምሥጢር አለ፤ በሞት ላይ ሥልጣን የነበረውን ዲያብሎስን ደምስሶታልና፡፡ እግዚአብሔር ሰው የሆነውና የሚያሳፍር የመስቀልን ሞት ሳይቀር የሞተው ለዚሁ ነው፡፡ “መልአከ ሞትን በሞቱ ይሽረው ዘንድ ይኸውም ሰይጣን ነው” (ዕብ.፪፥፲፬)፡፡ በማለት ሐዋርያው እንደተናገረ ጥንተ ጠላት ዲያብሎስ ተሻረ፡፡ “ከሲኦል እጅ እታደጋቸዋለሁ፥ ከሞትም እቤዣቸዋለሁ ሞት ሆይ፥ መውጊያህ ወዴት አለ? ሲኦል ሆይ ድል መንሣትህ  ወዴት አለ? ደስታህ ከዓይኖችህ ተሰወረች።” (ሆሴ.፲፫፤፲፬) በማለት ነቢዩ ሆሴዕ እንደተነበየው፡፡

ጌታችን ሞትን በማጥፋት የዲያብሎስን ሥልጣን አስወገደበት፡፡ የታሠሩትን ነጻ ለማውጣት ራሱን ለሕማምና ለለሞት አሳልፎ ሰጠ፡፡ “ቅዱስ” እና “ፍጹም” በመሆን እግዚአብሔርን እንድንመስለው ጸጋ ተሰጥቶናል፡፡ ዲያብሎስ ሊሳለቅብንና ሊፈትነን ዘወትር እረፍት ባይኖረውም አዛዣችን መሆን ግን አይችልም፡፡ ለኃጢአት መንበርከክ፣ ለኃጢአት ተገዢ መሆን አብቅቷል፡፡ ግብጻዊው ቅዱስ መቃርዮስም “የመድኃኒታችን (የአዳኛችን) ንጽሕት ፈቃድ ከፍትወታትና ከኃጢአት ነጻ አውጥታናለች” ብሏል፡፡

በክርስቶስ የተፈጸመ ዕርቅ

የሥግው ቃል ክርስቶስ ሰው የመሆኑ ውጤት የእግዚአብሔርና የሰው ዕርቅ ነው፡፡ ነባቤ መለኮት ቅዱስ ጎርጎርዮስ ይህንን ሲያስረዳ “እግዚአብሔር ጨካኙን ገዢ ድል በመንሣት እኛን ነጻ አውጥቶ በልጁ በኩል ከራሱ ጋር አስታረቀን” ብሏል፡፡ በኃጢአት ምክንያት ሰዎች የእግዚአብሔር ጠላት ሆኑ፤ በሥርየተ ኃጢአትና ይቅርታን በማግኘት ወይም በክርስቶስ ቤዛነት ግን ወዳጆቹ ከመሆንም ባለፈ ልጆቹ ሆኑ፡፡

ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ በመሆን በሰውና በእግዚአብሔር መካከል መካከለኛ የሆነ እርሱ ሰላምን አወረደ፡፡ “ሁሉንም በእርሱ ይቅር ይለው ዘንድ በመስቀሉ ባፈሰሰው ደም በምድርና በሰማያት ላሉ ሰላምን አደረገ፡፡ እናንተንም ቀድሞ በሐሳባችሁና በክፉ ሥራችሁ ከእግዚአብሔር የተለያችሁና ጠላቶች ነበራችሁ፡፡ አሁን ግን በፊቱ ለመቆም የተመረጣችሁና ንጹሓን፣ ቅዱሳንም ያደርጋችሁ ዘንድ፣ በእርሱም ፊት ያቀርባችሁ ዘንድ በሥጋው ሰውነት በሞቱ ይቅር አላችሁ።” (ቆላ.፩፥፳-፳፪) በማለት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ዕርቅ መፈጸሙን ይነግረናል፡፡ ይህ ሲባል በሰው በደል ምክንያት ለሰው ልጅ የተፈጠሩ ፍጥረታት ከሰው ጋር ተጣልተውና ተለያይተው ነበር፡፡ በክርስቶስ ሰው መሆንም በዋናነት በነፍስና በሥጋ፣ በሰውና በመላእክት፣ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የነበረው የጥል ግድግዳ ፈርሶ ለሁሉም ሰላምን አደረገ፡፡

ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ በምን ዓይነት መሥዋዕት እንደ ታረቀን ሲገልጽ “የሚሠዋ በግ እርሱ ነው፤ የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው፡፡ በፈቃዱ መከራን በሥጋው የተቀበለ፣ መከራንም ሁሉ የታገሰ እርሱ ነው፡፡ እንደ በግ ሊሠዋ መጣ፤ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንዳይናገር አልተናገረም፤ በአንደበቱ ሐሰት አልተገኘበትም” በማለት እንዲሁ ወዶንና ሁሉንም መንገድ እርሱ ተጉዞ እንደ ታረቀን አስተምሯል፡፡ እርሱ ስለ እኛ ሞቶ፣ ሞትንም ድል አድርጎ በመነሣቱ ለኃጢአታችን ካሣ ተከፈለልን፤ ወይም ይቅር ተባልን፣ ዓለም በደሙ ነጻች፣ ዘለዓለማዊነት ተሰጠን፣ ቤተ ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ምሪት ተመሠረተች፡፡ በክርስቶስ ተቤዥተው በመንፈስ ቅዱስ የተቀደሱት ፍጥረታት ዘወትር ለእግዚአብሔር የምስጋናን መሥዋዕት የሚያቀርቡና የመሥዋዕታቸውንና የአምልኮአቸውን ዋጋ የሚያገኙ ሆኑ፡፡

ክርስቶስ በመስቀል ላይ ያደረገልንን እናውቀዋለን፤ በደሙ ተቤዥቶናልና፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ “ስለ ኃጢአታችን  የተሰቀለውን፣ ሊያስነሣንና ሊያጸድቀን የተነሣውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከሙታን ተለይቶ በአስነሣው ስለምናምን ስለ እኟም ነው እንጂ” ብሎ ገለጸው፡፡ (ሮሜ.፬፥፳፭)፡፡ “ሊያስነሣንና ሊያጸድቀን የተነሣውን” ሲል ምን ማለቱ ነው? እርሱ ባይሞትልንና ስለ ብዙዎች ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሙን ባያፈስልን ኖሮ አሁንም ድረስ በዲያብሎስ ሥር ተገዢዎች እንሆን ነበር፡፡ (ማቴ.፳፮፥፳፰)፡፡ እርሱ በተዋሐደው ሥጋ ሞቶ ተነሣ፤ ሞትንም ድል አደረገ፡፡ ይህ ባይሆን ኖሮ ግን ጽድቅ አይኖርም፤ ዕርቅ አይኖርም፤ ቅድስና አይኖርም፡፡ ሁሉም የኖሩት በሞቱና በትንሣኤው መሠረትነት ላይ ነው፡፡ እርሱ ሰው ሆኖ ወደዚህ ዓለም ባይመጣና ልጅነትን ባይመልስልን በሞቱ ትንሣኤያችንን ባያውጅልን ኖሮ የአካለ ክርስቶስ ብልቶች አንሆንም፤ ድኅነትም የለም፡፡ “አካልም አንድ እንደ ሆነ ብዙም ብልቶች እንዳሉበት ነገር ግን የአካል ብልቶች ሁሉ ብዙዎች ሳሉ አንድ አካል እንደ ሆኑ፥ ክርስቶስ ደግሞ እንዲሁ ነው፤ … እኛ ሁላችን በአንድ መንፈስ አንድ አካል እንድንሆን ተጠምቀናልና።” (፩ቆሮ.፲፪፥፲፪-፲፫) እንዲል፡፡ በጥምቀት አንድ ስለመሆናችንም ሲገልጽ “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋል” ተብለናል፡፡ (ገላ.፫፥፳፯)፡፡

እኛ የክርስቶስ ነን፤ የእርሱ አካል ብልቶች ነን፡፡ የምንጠመቀው መጠመቅም ከእርሱ ሞትና ትንሣኤ የሚያሳትፍ ነው፡፡ (ሮሜ፮፥፫-፲፩)፡፡ በዚህም ምክንያት በጥምቀት ሦስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ ብለን ረቂቅ ልብሰ ብርሃን ለብሰን እንወጣለን፡፡ (ለሞቱ ምሳሌ እንዲሆን) ከጠለቅንበት ውኃ በመውጣት ቀና እንላለን፤ ይህም በእግዚአብሔር የሚኖረንን አዲስ ሕይወት የሚጠቁም ነው፡፡

መጽደቅ ማለት ከወልደ እግዚአብሔር ጋር መታረቅ፣ ከዚያም የእግዚአብሔርን ልጅነት ማግኘት ነው፡፡ “አባ አባት ብለን የምንጮህበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና። የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ያ መንፈስ ራሱ ከመንፈሳችን ጋር ይመሰክራል። ልጆች ከሆንን ወራሾች ደግሞ ነን፤ ማለት የእግዚአብሔር ወራሾች ነን፥ አብረንም ደግሞ እንድንከብር አብረን መከራ ብንቀበል ከክርስቶስ ጋር አብረን ወራሾች ነን።” (ሮሜ.፰፥፲፭-፲፯)፡፡ ክርስቶስ ሰው ሆኖ  የተወሰደብንን ክብር ልጅነት ሰጠን፣ ወደ ጥንተ ርስታችን ወደ ገነት መለሰን፤ ይህ ሁሉ የሆነውና የታየው በሞቱና በትንሣኤው ነውና የክርስቶስን ትንሣኤ የትንሣኤያችን ማረጋገጫ ማኅተም እንለዋለን፡፡

ይቆየን፡፡

ሥርዓተ ሰሙነ ሕማማት

በሊቀ ጠበብት ሐረገወይን አገዘ

ክፍል ሁለት

ጸሎተ ሐሙስ፡-

በብሉይ ኪዳን የቂጣ በዓል የሚለውን ትርጉም ከመሰጠቱ በተጨማሪ ጌታችን ምሥጢረ ቁርባንን ከምሥጢረ ጸሎት ጋር አዋሕዶ የገለጠበት ዕለት ስለሆነ ታላቅ የምሥጢር ቀን ነው፡፡

በዚህ ዕለት ስግደቱ፣ ጸሎቱ፣ ምንባባቱ እንደተለመደው ይከናወናሉ፡፡ ለየት ያለው ሥርዓት መንበሩ/ታቦት/ ጥቁር ልብስ ይለብሳል፣ ጸሎተ ዕጣን ይጸለያል፣ ቤተ ክርስቲያኑ በማዕጠንት ይታጠናል፡፡

በዘጠኝ ሰዓት ዲያቆኑ ሁለት ኩስኩስቶችን ውኃ ሞልቶ ያቀርባል፣ አንዱ ለእግር፣ አንዱ ለእጅ መታጠቢያ፡፡ ጸሎተ አኰቴት የተባለ የጸሎት ዓይነት ተጸልዮ፣ ወንጌል ተነቦ ውኃው በካህኑ /በሊቀ ጳጳሱ/ እጅ ተባርኮ የሕጽበት እግር ሥርዓት ከካህናት እስከ ምእመናን፣ ከወንዶች እስከ ሴቶች በካህኑ አስተናጋጅነት ይከናወናል፡፡

ሥርዓተ ኅጽበቱ የሚከናወነውም በውኃ ብቻ ሳይሆን የወይራና የወይን ቅጠልንም ለሥርዓቱ ማስፈጸሚያነት እንጠቀምባቸዋለን፡፡ ምሥጢሩም የሚከተለውን ይመስላል፡፡

ወይራ ጽኑዕ ነው፡፡ ክርስቶስ ጽኑዕ መከራ መቀበሉን ከማስረዳቱ በተጨማሪ እኛም /የሚያጥበውና የሚታጠበው ክርስቲያን/ መከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ነው፡፡ የወይኑ ቅጠል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወይን የተመሰለ ደሙን አፍስሶ ለምእመናን ሕይወት መጠጥ ይሆናቸው ዘንድ መስጠቱን ለማዘከር ነው፡፡ (ማቴ.፳፮፥፳፮)፡፡

ይህም ሥርዓት ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብ ያሳየውን የተግባር ትምህርት ለምእመናን ለማሳየት ነው፡፡ (ዮሐ.፲፫፥፲፬)፡፡ሊቃውንትም በቀኝና በግራ “ሐዋሪያቲሁ ከበበ እግረ አርዳኢሁ ሐፀበ” እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ይህ ሥርዓት ከተጠናቀቀ በኋላ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖ ቅዱስ ሥጋውን፣ ክቡር ደሙን ምእመናን ይቀበላሉ፡፡

የጸሎተ ሐሙስ ቅዳሴ፡-

ቅዳሴው የሚከናወነው በተመጠነ ድምጽ ነው፡፡ ደወሉ የጸናጽል ድምጽ ነው በቀስታ ስለሚጮህ ነው፡፡ የድምጽ ማጉያ አይጠቀሙም፤ ምክንያቱም ዲያቆኑና ካህኑ ዜማውን በቀስታ የሚሉት ይሁዳ በምሥጢር ጌታችንን ማስያዙን ለመጠቆም ሲሆን በሌላ በኩል የዘመነ ብሉይ ጸሎት ዋጋው ምድራዊ እንደነበር ለማስታወስ ነው።

በመቀጠል ክቡር ይእቲ፣ ዕጣነ ሞገር ዝማሬ የተባሉ የድጓ ክፍሎች ተዘምረው አገልግሎቱ ይጠናቀቃል፡፡ ሕዝቡም ያለ ኑዛዜና ቡራኬ ይሰናበታሉ፡፡

ዕለተ ዐርብ ነግህ፡-

ዕለተ ዐርብ የአዳምን ነጻነት ለመመለስ የአዳምን ዕዳ በደል አምላካችን የተሸከመበት ዕለት፣ የኀዘን ዕለት፣ የድኅነት ዕለትም ነው፡፡ በዚሁ ዕለት ሁሉም ነገር እንደተለመደው ይከናወናል፡፡ መሪው እዝል ይመራል፣ ሕዝቡ ይከተላል፣ አራቱ ወንጌላት ይነበባሉ፡፡ በየመሐሉ “ወጸቢሆ ተማከሩ ሊቃነ ካህናት፤ ሲነጋም ሊቃነ ካህናት ተማከሩ” የሚለው ዜማ በመሪ፣ በተመሪና በሕዝብ ተሰጥዎ ይከናወናል፡፡  ምንባቡም፣ ስግደቱም፣ ድጓውም እንደአለፈው ይቀጥላል።

በሦስት ሰዓት፡-

ሥዕለ ስቅለቱ፣ መስቀሉ፣ ወንጌሉ፣ መብራቱ፣ ጽንሐሑ በመቅደሱ በር ላይ ይዘጋጃል፤ ዲያቆኑ በቃለ ማኅዘኒ በሚያሳዝን ቃል ግፍኦሙ እግዚኦ ለእለ ይገፍኡኒ ይላል፡፡ ካህናቱና ምእመናኑም በዜማ እየተቀበሉ ይሰግዳሉ፡፡ ምስባክ ተሰብኮ አራቱ ወንጌላት ይነበባሉ፡፡ በየመሐሉ የሰዓቱ ድጓ ይቃኛል፡፡

ስድስት ሰዓት፡-

የዕለቱ መሪ እዝል ይመራል፣ ሦስቱ ካህናት ጽንሐሑን ይዘው ከርቤ እያጠኑ ዲያቆናት መብራት እያበሩ ለመስቀልከ ንስግድ እያሉ ያዜማሉ፣ ምእመናንም ዜማውን እየተቀበሉ ይሰግዳሉ፡፡ ከዚያም ዲያቆኑ ቀነውኒ እደውየ ወእገርየ የሚለውን ምስባክ ሰብኮ አራቱ ወንጌላት ይነበባሉ፣ በየመሐሉ ድጓው ይዜማል፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ምእመናን ይቀመጣሉ፣ ሦስቱ ካህናት ጥቁር ልብስ ለብሰው በሚያሳዝን ዜማ አምንስቲቲ ሙኪርያ አንቲ ፈሲልያሱ፣ ጌታዬ ሆይ ስለ እኔ ሞትህ ወዮ እኔ ልሙትልህ እያሉ ሦስት ጊዜ ያዜማሉ፡፡

ሕዝብ ይቀበላል፣ በዚያው አያይዘው ተዘከረነ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ እያሉ በዜማ ይጸልያሉ ሕዝቡ ይቆማል ሥርዓተ ስግደቱም ይከናወናል፡፡

በዘጠኝ ሰዓት፡-

ሌላው እንደተለመደው ሆኖ ኦ ዘጥዕመ ሞተ በሥጋ ሦስት ጊዜ ካህናቱ በዜማ ይሉታል፣ ምእመናኑም ይቀበላሉ፡፡ ምስባክ ተሰብኮ አራቱ ወንጌላት ይነበባሉ፣ ስግደት እንደተለመደው ነው፡፡ በሦስት ሰዓት፣ በስድስት ሰዓት፣ በዘጠኝ ሰዓት፣ ወንጌላቱ ተነበው እንዳለቁ ለምእመናን ትምህርት ወንጌል ይሰጣል፡፡ ይህ ግን እንደ ቋሚ ሥርዓት ሳይሆን እንደ ሁኔታው አመቺነት ነው፡፡

አሥራ አንድ ሰዓት፡-

ካህናት በአራቱ ማዕዘን ቁመው አራት መቶ እግዚኦታ ያደርሳሉ፣ ዕለቱን የሚመለከቱ መዝሙራት ተመርጠው ይነበባሉ፡፡ ንሴብሖ እየተባለ ቤተ መቅደሱን በመዞር በከበሮ በጸናጽል በሕማሙ ያዳነን እግዚአብሔር ይመሰገናል፡፡ ዑደት የሚደረገው ሥነ ስቅለቱን በመያዝ ነው፡፡ ምእመናን በሰሙነ ሕማማት የሠሩትን ኃጠአት እየተናዘዙ በካህናት አባቶች ንስሓ ይቀበላሉ፣ በወይራ ቅጠልም ቸብ ቸብ ይደረጋሉ፤ የመከራው ተሳታፊዎች መሆናቸውን ለመግለጥ ነው፡፡ ወይራ ጽኑዕ ነው፣ የተቀበልከው መከራም ጽኑዕ ነው እኛም ይህን መከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ነው፡፡ በታዘዙት መሠረትም ስግደታቸውን ያጠናቅቃሉ፡፡

ከዚያ በኋላ በካህኑ ኑዛዜ ምእመናን ወደ ቤታቸው ይሰናበታሉ፡፡ መስቀል መሳለም አሁንም የለም፣ የቻለ ከሐሙስ ጀምሮ አሊያም ከዐርብ ማታ ጀምሮ እስከ ዕለተ ትንሣኤው ድረስ ያከፍላል/ይጾማል/፡፡ የተጀመረውም በዕለተ ስቅለቱ በሐዋርያትና በእመቤታችን እንደሆነ አበው ያስተምራሉ፡፡

ቀዳም ሥዑር፡-

የማትጾመዋ ቅዳሜ ስለምትጾም “ሥዑር/የተሻረች/ ትባላለች፣ በዓል መሻርን ግን አያመለክትም፡፡ ቀዳም ሥዑር በጾም ምክንያት የተሻረችው ቀዳሚት ሰንበት በሰንበት ሌሊት ሥርዓቱ የሚጀምረው በመኀልየ ሰሎሞን ምንባብ ነው፡፡ ማኅሌቱም እዝሉ እየተቃኘ፣ እየተመለጠነ፣ እየተዘመመ፣ እየተመረገደና እየተጸፋ ያድራል፡፡ ጠዋት አቡን መሥዋዕት ውዳሴ ማርያም ዜማ ተደርሶ ወለመልአከ ሕይወትሰ ሰቀልዎ በሚለው ሰላምታ ይጠናቀቃል፡፡ ገብረ ሰላም በመስቀሉ እየተባለ እየተዘመረ ቄጤማውም ቤተ መቅደሱን ዞሮ በካህኑ ተባርኮ ለምእመናን ይታደላል፡፡

የቄጠማው አመጣጥና ምሥጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ /በጥፋት ውኃ/ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሰረችው ቄጠማ ይዛ በመግባት ነው፡፡

ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጠአት ውኃ ጎደለ፣ የኃጠአት ውኃ ጠፋ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ፣ ታወጀ በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበስሩበታል፡፡ በአጠቃላይ ሥርዓተ ሕማማት ብለው የተለየ ሥርዓት አውጥተው አባቶቻችን ተግተው ያቆዩልንን ሥርዓተ መላእክት ልንጠብቀውም ልንጠቀምበት ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ሰባቱ አጽርሐ መስቀል”

በቀሲስ ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ እና የአምልኮ ሥርዓት ከሆሣዕና ጀምሮ እስከ ትንሣኤ ያሉት ቀናት ሰሙነ ሕማማት ይባላሉ፡፡ ከሆሣዕና ማግስት ሰኛ ጀምሮ እያንዳንዱ ቀናት ስያሜ አላቸው፡፡ እነሱም፡- ሰኞ መርገመ በለስ፣ አንጽሖተ ቤተ መቅደስ፣ ክሰኞ፡- የጥያቄ ቀን፣ የትምህርት ቀን ረቡዕ፡- ምክረ አይሁድ፣ የዕንባ ቀን፣ የመልካም መዓዛ ቀን፣ ሙስ፡- ሕጽበተ እግር፣ የምሥጢር ቀን፣ ጸሎተ ሐሙስ፣ ዐርብ፡– ስቅለት፣ ቅዳሜ፡- ቀዳም ሥዑር በመባል በእያንዳንዳቸው ቀን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን የፈጸማቸው ምሥጢራትና የተቀበለው መከራ እየታሰበ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት ታስበው ይውላሉ፡፡

በቤተ  ክርስቲያን  ግብረ  ሕማም  የተሰኘው  መጽሐፍ  እየተነበበ  ሌሎችም  መከራውን፣ ሕማሙን፣ መሰቀል፣ መሞቱን የሚያወሱ የጸሎት ክፍሎች እየተደገሙና እየተዜሙ ከሌሊቱ ጀምሮ ቀኑን ሙሉ እየተሰገደ ሥርዓተ አምልኮ ይፈጸማል፡፡ በዕለተ ዐርብም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተገረፈበት፣ መስቀሉን ተሸክሞ የቀራንዮን ተራራ እየወደቀ እየተነሣ እንዲወጣ የተደረገበትና መከራ መስቀሉን የተቀበለበት ቀን በመሆኑ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ በተሰበረ ልብ እና በትሑት ሰብእና ሆነው በመስቀል ላይ የተፈጸሙትን ጸዋትወ መከራ እያሰቡ በስግደት ይውላሉ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሆኖ የተናገራቸው ቃላት በቤተ ክርስቲያናችን አስተምሮ ሰባት ናቸው፡፡ እነሱም በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱ ሲሆን ሰባቱ አጽርሐ መስቀል በሚል የሚታወቁ ናቸው፡፡ ቀጥለንም በዝርዝር እንመለከታቸዋለን፡-

ኛ “ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ፤አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ”፡- ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሳለ በዘጠኝ ሰዓት የተናገረው ቃል እንደሆነ በወንጌል ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ “በዘጠኝ ሰዓትም ጌታችን ኢየሱስ ኤሎሄ ኤሌሄ ላማ ሰበቅታኒ ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸ፡፡ ይኸውም አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ? ማለት ነው፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት በሰሙ ጊዜ ይህስ ኤልያስን ይጠራል አሉ” (ማቴ.፳፯፥፵፭)እንዲል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ ብሎ የተናገረበት መሠረታዊ ሐሳብ፡- ያችን የድኅነት ቀን ከአምስት ሺ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ያለችውን ዕለተ ዓርብ በተስፋ ይጠባበቅ የነበረውን አዳምን ወክሎ እንደሆነ አበው ያስረዳሉ፡፡ (ማቴ.፳፯፥፵፭ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡  በመሆኑም  አምላኬ  አምላኬ  ያለው  በአዳም ተገብቶ  እንደሆነ  መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እንዲሁም አምላኬ አምላኬ ያለው ሰውነቱን ሲገልጥ ነው፡፡ ይህም ፍጹም አምላክነቱንና ፍጹም ሰውነቱን ማለት ነው፡፡

ኛ “ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ”፡- ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደል ሳይኖርበት እንደ በደለኛ ተቆጥሮ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ነበር የተሰቀለው፡፡ “ከእርሱ ጋርም ሁለት ወንበዴዎችን አንዱን በቀኙ አንዱን በግራው ሰቀሉ፡፡ መጽሐፍ ከዐመፀኞች ጋር ተቈጠረ ያለው ተፈጸመ” (ማር.፲፭፥፳፯) ይላልና፡፡

በቀኝ በኩል የተሰቀለው ወንበዴ ጌታችንን “አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ›” አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው ‹‹እውነት እልሃለሁ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ፡፡›› (ሉቃ.፳፫፥፵፫)፡፡

ኛ “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ”፡-  “ያን ጊዜም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድምጹን ከፍ አድርጎ አባት ሆይ ነፍሴን በአንተ እጅ አደራ እሰጣለሁ ብሎ ጮኸ፤ ይህንም ብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ሉቃ.፳፫፥፵፮)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” በማለት የተናገረው ቃል የተሰቀለው እርሱ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነና የአብ የባሕርይ ልጁ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ይህም እግዚአብሔር አብና እግዚአብሔር ወልድ በአካል የተለያዩ መሆናቸውን መስቀል ላይ የተሰቀለው ወልድ አብን “ነፍሴን ተቀበል” ብሎ የሚናገር እንጂ ራሱ አብ አለመሆኑን በግልጽ የሚያስረዳ ነው፡፡

፬ኛ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው”፡- ምንም በደል ሳይኖርበት አይሁድ በክፋት ተነሳስተው መከራ አጸኑበት፤ ያን ሁሉ የግፍ ግፍ በጭካኔ የተሞላ መከራ ሲያደርሱበት ልባቸውን ዲያብሎስ ስላደነዘዘው የሚራራ ልብ አጡ፡፡ በዚያንም ጊዜ መምህረ ይቅርታ ቸሩ አምላካችን  ለሠቃዮቹ “አባት  ሆይ  የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው አለ” (ሉቃ.፳፫፥፴፬)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደለኞች ይቅርታን ያገኙ ዘንድ ይቅር በላቸው አለ፡፡ ልመናውንም ያቀረበው ወደ ባሕርይ አባቱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ጋር ደግሞ በባሕርይ፣ በህልውና፣ በአገዛዝ፣ በፈቃድ አንድ ናቸው፡፡ እንዲሁም የሰውን ባሕርይ ባሕርይ አድርጎ ፍጹም ሰው እንደሆነ ሲያስረዳ ነው፡፡ ይህም በደለኞችን ከራሱ ጋር ያስታረቀበት የፍቅር ድምጽ ነው፡፡

አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው ማለቱ አባት ሆይ ብሎ የባሕርይ ልጅነቱን ከመግለጹ በተጨማሪ ይቅር በላቸው ማለቱ ጠላትን ይቅር ማለት የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ የመሆኑ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ምክንያቱም ጠላቶቻችሁን ውደዱ ብሎ ያስተማረ እርሱ ብቻ ነውና፡፡

፭ኛ “እነሆ ልጅሽ እናትህ እነኋት”፡- “ጌታችን ኢየሱስም እናቱንና የሚወደውን ደቀ መዝሙሩን ቆመው ባያቸው ጊዜ እናቱን ‘አንቺ ሆይ እነሆ ልጅሽ’ አላት፡፡ ከዚህም በኋላ ደቀ መዝሙሩን ‘እናትህ እነኋት’ አለው፡፡ ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ተቀብሎ ወደ ቤቱ ወሰዳት”(ዮሐ.፲፱፥፳፮)፡፡ ደቀ መዝሙሩ ተብሎ የተጠቀሰው ጌታችን ይወደው የነበረ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊው ነው፡፡ ይህንንም የጻፈው እርሱ ነው (ዮሐ.፳፩፥፳፬)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ከዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት አንዱ ቢሆንም ሐሙስ ማታ እረኛው ሲያዝ ከተበተኑት በጎች ጋር አብሮ አልሸሸም፡፡ በዚያች በአስጨናቂዋ ሰዓት ከጌታችን ጋር እስከ እግረ መስቀሉ ተጓዘ፡፡ የክርስቶስ ፍቅር ፍርሃቱን ሁሉ አርቆለት የአይሁድን ቁጣና ዛቻ ሳይፈራ ጸንቶ በመቆሙ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለእኛ ሁሉ በእርሱ በኩል ተሰጠችን፡፡ እናታችን ድንግል ማርያም ሁል ጊዜም ቢሆን ከእግረ መስቀሉ ሥር ለሚገኙ፣ ልባቸው ቀራንዮን ለሚያስብ ሁሉ እናት እንድትሆን እነርሱም ልጆቿ እንዲሆኑ በቅዱስ ዮሐንስ በኩል ተሰጥታናለች፡፡

በመሆኑም “እነሆ ልጅሽ እናትህ እነኋት” የሚለው የመስቀሉ ቃል በመስቀል ላይ የተከፈለልንን  ዋጋ  አስበን  በእርሱ  አምነን  በምግባር  ታንጸን  እንደ  ፈቃዱ  በምንኖር ክርስቲያኖችና ለድኅነታችን ምክንያት በሆነች በእመ አምላክ በድንግል ማርያም መካከል የእርሷ እናትነት፣ የእኛ ልጅነት የተመሠረተበት የፍቅር ቃል ነው፡፡

ኛ “ተጠማሁ”፡- “ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ሁሉ እንደተፈጸመ ባየ ጊዜ የመጽሐፍ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‘ተጠማሁ’ አለ” (ዮሐ.፲፱፥፳፰)፡፡

ውኆችን በእፍኙ የሰፈረ፣ የባሕር አሸዋን የቆጠረ፣ ውኆችንም ጠርቶ በምድር ፊት ላይ የሚያፈሳቸው፣ የባሕር ጥልቀትንና ዳርቻን የወሰነ፣ የኤርትራን ባሕር እንደ ግድግዳ ያቆመ አምላክ “ተጠማሁ” ብሎ ጮኸ፡፡ (ኢሳ.፵፥፲፪፣ አሞ.፱፥፮)፡፡

“የተጠማ ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ በእኔም የሚያምን መጽሐፍ እንደተናገረ የሕይወት ውኃ ምንጭ ከሆዱ ይፈልቃል” (ዮሐ.፯፥፴፯) በማለት እርሱ የሕይወት ውኃ እንደሆነ ተናገረ፡፡ አምላክ ሲሆን “ተጠማሁ” ብሎ መጮኹ ስለምንድን ነው ብለን ቅዱሳት መጻሕፍትን ስንመረምር፡- አንደኛ የመከራውን ጽናት፣ ከሚነገረው በላይ መከራውን እንዳጸኑበት የሚያሳይ ሲሆን፤ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ እርሱ የተጠማው የሰውን መዳን ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በዚያን ወቅት እንኳ ከክፉ ሥራው ተመልሶ የሚጸጸት፣ የሚራራ፣ ንስሓ የሚገባ ሰው በማጣቱ መድኃኒት እርሱ ቀርቦ ሳለ የሰው ልጅ ባለማስተዋሉ ወደ እርሱም በፍቅር ባለመቅረቡና ባለመመለሱ ተጠማሁ አለ፡፡

ኛ “ሁሉ ተፈጸመ”፡- ”ጌታችን ኢየሱስም ሆምጣጤውን ቀምሶ ሁሉ ተፈጸመ አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ዮሐ.፲፱፥፴)፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕተ ዐርብ በመስቀል ላይ ሳለ ‘ተፈጸመ’ ብሎ መናገሩ ብዙ ትርጉም ያለው ቃል ነው፡፡ እነርሱም፡-

በነቢያት ስለ እኔ የተነገረው ትንቢት፣ የተመሰለው ምሳሌ፣ በቅዱሳን አበው የተቆጠረው ሱባኤ፣ ጊዜው ደርሶ የአዳም ተስፋ ተፈጸመ፡፡ የሰው ልጅ በዲያብሎስ አገዛዝ በሞትና በጨለማው ሥልጣን፣ በአጋንንት ወጥመድ ታስሮ የሚኖርበት የፍዳ ዘመን አለቀ ተፈጸመ፡፡ በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰማይና በምድር መካከል ቆሞ የነበረው የጥል ግድግዳ ፈረሰ፣ የተጻፈው የዕዳ ጽሕፈት ተደመሰሰ፣ የሰው ልጅ ዕዳ በደል ተከፈለ በአምላክ የቤዛነት ሥራ ሁሉ ተፈጸመ ማለት ነው፡፡

እነዚህ  ከአንድ  እስከ  ሰባት  የጠቀስናቸው  የመስቀል  ላይ  ድምጾች  ናቸው፡፡  ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መራራውን መከራ እየተቀበለ የተናገራቸው የመጨረሻ ቃላቶቹ ናቸው፡፡ ወደዚህ ዓለም ሰው ሆኖ የመጣበትን ዓላማ አከናውኖ ሲጨርስ በመጨረሻ “ተፈጸመ ኵሉ” በማለት ነፍሱን ከሥጋው ለየ፡፡ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶም በሲኦል ባርነት ለነበሩት አዳምና ልጆቹ ነጻነትን ሰበከላቸው፡፡ በአካለ ሥጋ ደግሞ ወደ መቃብር ወርዶ ሙስና መቃብርን አጠፋልን፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን፡፡

ሥርዓተ ሰሙነ ሕማማት

ከሊቀ ጠበብት ሐረገወይን አገዘ

ሥርዓት ምንድነው?

“ወንድሞች ሆይ ከእኛ የተቀበለው ወግ ሳይሆን ያለ ሥርዓት ከሚሔድ ወንድም ትለዩ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እናዛችኋለን” (፪ኛ ተሰ.፫፥፮)፡፡

ሥርዓት የሥነ ፍጥረት ሕይወት ምሕዋር፣ መቆጣጠሪያ መሣሪያ ነው፡፡ የመዓልቱ በሌሊት የሌሊቱ በመዓልት በመሠልጠን ሥርዓተ ዑደትን እንዳይጥስና የመዓልቱ በመዓልት፣ የሌሊቱ በሌሊት እየተመላለሰ ዕለታዊ ግብሩን እንዲያከናውን ማንኛውንም ፍጡር ፈጣሪው በሥርዓት አሰማርቶታል፡፡(መዝ.፩፻፳፭፥፲፱-፳፬)፡፡

በተለይ መንፈሳውያን ልዑካን መንፈሳዊውን ተልእኮ ያለ ሥርዓትና ሕግ ማካሔድ እንደማይችሉና እንደማይገባም ሐዋርያው ሲያስተምር “ያለ ሥርዓት ከሚሔድ ወንድም ተለዩ” አለ፡፡

ስለሆነም በሰሙነ ሕማማት የሚከናወኑ ሃይማኖታዊ እሴቶች ከዚህ ኃይለ ትምህርት የተገኙ መሆናቸውን እያሰብን በሰሙነ ሕማማት የሚከናወኑ የሕማማት ሥርዓቶችን ቀጥለን እንመለከታለን፡፡

ሰሙነ ሕማማት፡-

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከዕለተ ትንሣኤ በፊት ያለውን ሳምንት ሰሙነ ሕማማት በማለት ታከብረዋለች፡፡ የዚህ ስያሜ መነሻም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መከራው፣ ሕማሙና ሞቱ የሚዘከርበት፣ ከአዳም እስከ ክርስቶስ የነበረው የዓመተ ፍዳ የዓመተ ኩነኔ ወቅትም የሚታሰብበት ስለሆነ ሰሙነ ሕማማት ተብሏል፡፡ የዚህ ጾም መነሻም በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ ተደንግጓል፡፡ ጥንታዊ ቀዳማዊ መሆኑም ይታወቃል፡፡

በሕማማት የማይፈቀዱ፡-

በዚህ በሰሙነ ሕማማት ሳምንት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለየት ያለ የአገልግሎት ሥርዓት ሠርታለች፡፡ ከጸሎተ ሐሙስ በቀር ቅዳሴ አይቀደስም፣ የዘወትር የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት የሆነው ጥምቀተ ክርስትና፣ ሥርዓተ ፍትሐት፣ ሥርዓተ ማሕሌት፣ ሥርዓተ ተክሊልና ሌሎችም የተለመዱ አገልግሎቶች አይካሔዱም፡፡ በመስቀል መባረክ፣ ኑዛዜ መስጠትና መቀበል፣ እግዚአብሔር ይፍታህ ማለት የለም፡፡ በአጠቃላይ ከዓመት እስከ ዓመት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አማካይነት ለምእመናን ይሰጡ የነበሩ መንፈሳውያት አገልግሎቶች አቁመው በሌላ ወቅታዊ ማለትም የጌታችን ሕማሙን፣ መከራውን፣ መከሰሱን፣ መያዙን፣ ልብሱን መገፈፉን፣ በጲላጦስ ዐደባባይ መቆሙን፣ መስቀል ላይ መዋሉን፣ ሐሞት መጠጣቱን እና ሌሎችም ለኃጢአተኛው የሰው ልጅ ሲባል የተከፈለውን ዕዳ በሚያስታውሱ አገልግሎቶች ይተካሉ፡፡

እነዚህንም ሥርዓታዊና ምሥጢራዊ የሰሙነ ሕማማት አገልግሎቶች ከዕለተ ሰኑይ እስከ ቀዳም ሥዑር ድረስ እንዴት እንደሚከናወኑ በአጭር በአጭሩ እንመለከታለን፡-

ዕለተ ሰኑይ/ሰኞ በነግህ፡-

ከሁሉም በፊት የዕለቱ ተረኛ አገልጋይ ቃጭል እየመታ ሦስት ጊዜ ቤተ ክርስቲያኑን ይዞራል፡፡ የሰባቱ ቀን ውዳሴ ማርያም፣ አንቀጸ ብርሃን፣ መዝሙረ ዳዊት በሙሉ ይጸለያል፡፡ በዕለቱ ተረኛ መምህር/መሪ ጌታ የዕለቱ ድጓ ይቃኛል፡፡ ድጓው ከዐራቱ ወንጌላት ምንባብ ጋር እንዲስማማ ሆኖ ነው የሚቃኘው፡፡ ድጓውን እየተቀባበሉ እያዜሙ ይሰግዳሉ፡፡ የድጓው መሪ መምህር ሰኞ በቀኝ ከሆነ ማክሰኞ በግራ በኩል ባለው መምህር ይመራል፡፡ እንዲህ እየተዘዋወረ ይሰነብታል፡፡ ድጓው ሦስት ጊዜ እየተመላለሰ ከተዘለቀ በኋላ፡-

      ለከ ኀይል ክብር ወስብሐት

      ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም

       አማኑኤል አምላኪየ ለከ ኀይል

       ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እከ ለዓለመ ዓለም

       ኦ እግዚእየ ኢየሱስ ክርስቶስ ለከ ኀይል

       ክብር ወስብሐት ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም

      ኀይልየ ወጸወይንየ ውእቱ እግእዚየ

       እስመ ኮንከኒ ረዳኢየ እብል በአኮቴት

እየተባለ በቀኝ በኩል ስድስት፣ በግራ በኩል ስድስት ጊዜ እየተዜመ ይሰገዳል፡፡ በድምሩ ፲፪ ጊዜ ማለት ነው፡፡ በዚያው ልክ አቡነ ዘበሰማያት በዜማ/በንባብ/ ይደገማል፡፡ ከዚያ በመቀጠልም፡-

       ለአምላክ ይደሉ ክብር ወስብሐተ ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም

       ለሥሉስ ይደሉ ክብር ወስብሐተ ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም

      ለእዘዙ ይደሉ ክብር ወስብሐተ ወእዘዝ እስከ ለዓለመ ዓለም

      ለመንግሥቱ፣ ለሥልጣኑ፣ ለምኩናኑ፣ ለኢየሱስ፣ ለክርስቶስ፣ ለሕማሙ ይደሉ

እያሉ በቀኝ በግራ እየተቀባበሉ ይሰግዳሉ፡፡ በመቀጠል የነግሁ ምንባብ መነበብ ይጀምራል፡፡ በመጨረሻም ተአምረ ማርያምና ተአምረ ኢየሱስ ይነበባሉ፡፡ ከዚያ ከዳዊት መዝሙር ምስባክ ተሰብኮ የሰዓቱ ወንጌል ከተነበበ በኋላ ጸልዩ በእንተ  ጽንዓ ዛቲ የተባለው በካህኑ ሲነበብ ምእመናንም አቤቱ ይቅር በለን እያሉ በመስገድ ይጸልያሉ፡፡

ከዚያም ሁለተኛው ሥርዓተ ስግደት ይጀመራል፡፡ ዜማው የሚጀምረው አሁንም በቀኝ በግራ በመቀባበል ነው፡፡ አንዱ ይመራል፣ ሌላው ይቀበላል፡፡ እንዲህ በማለት፡-

      ኪርያላይሶን/፭ ጊዜ/በመሪ በኩል

      ኪርያላይሶን /፪ ጊዜ/ ዕብኖዲ ናይን በተመሪ በኩል

      ኪርያላይሶን ታኦስ ናይን

      ኪርያላይሶን ማስያስ ናይን

      ኪርያላይሶን ኢየሱስ ናይን

      ኪርያላይሶን ክርስቶስ ናይን

     ኪርያላይሶን አማኑኤል ናይን

     ኪርያላይሶን ትስቡጣ ናይን

በዚሁ መልኩ አንድ ጊዜ ከተዘለቀ በኋላ እንደገና ይደገማል፡፡ በመጨረሻም በቀኝ በግራ በማስተዛዘል አርባ እንድ ጊዜ እየተዜመ ይሰገዳል፡፡ ከላይ የተገለጹት የጌታችን ኅቡአት ስሞች ናቸው፡፡ ኪርያላይሶን ማለት አቤቱ ይቅር በለን ማለት ነው፡፡

በመቀጠል መልክአ ሕማማት በሊቃውንቱ ይዜማል፡፡ ከዚያም ካህኑ ፍትሐት ዘወልድ፣ ጸሎተ ቡራኬ፣ ወዕቀቦሙ፣ አ ሥሉስ ቅዱስ፣ ኦ ማኅበራኒሁ ለክርስቶስ፣ ነዋ በግዑ የተሰኙ ምንባባትን እያፈራረቁ ያነባሉ፡፡ ካህኑም በጸሎታቸው ፍጻሜ ፵፩ ጊዜ ኪራላይሶን በሉ ብለው መልእክት ያስተላልፋሉ፡፡ ሕዝቡም መልእክቱን ተቀብሎ ይጸልያል፡፡ ዲያቆኑም “ሑሩ በሰላም እግዚአብሔር የሀሉ ምስሌክሙ፣ ንዑ ወተጋብኡ ውስተ ቤተ ክርስቲያን በጊዜ ሠለስቱ ሰዓት ብሎ ያሰናብታል፡፡

አሁን የተመለከትነው ሥርዓት ሰኞ በነግህ/በጥዋት/ የሚከናወን ነው፡፡ በ፫፣ በ፮፣ በ፱፣ በ፲፩ ሰዓት የሚከናወነው ሥርዓትም አሁን በተመለከትነው መሠረት ነው፡፡ የሚለያዩት ምንባባቱ ብቻ ናቸው፡፡ የሰሙነ ሕማማት ዜማም ከሰኞ እስከ ረቡዕ ግእዝ፣ ሐሙስ አራራይ፣ ዐርብና ቅዳሜ እዝል ነው፡፡ አሁን በተመለከትነው መሠረት ሰኞ፣ ማክሰኛ፣ ረቡዕ ከምንባባቸው በቀር ከላይ በተመለከትነው አኳኋን ሥርዓታቸው ይፈጸማል፡፡

ይቆየን፡፡

ምንጭ፡- ከስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ከመጋቢት ፳-፳፬ ቀን ፳፻፪ ዓ.ም

 “ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት…” (ቅዱስ ያሬድ)

በቀሲስ ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

ሆሣዕና  በዕብራይስጥ  ሆሼዕናህ የሚል ሲሆን  ትርጒሙም “አቤቱ አሁን አድን” ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና መሠረት ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታ አሉት፡፡ ሳምንታቱም የየራሳቸው ስያሜ አላቸው፡፡ ለማስታወስ ይረዳን ዘንድ ስንቃኛቸውም የመጀመሪያው ሳምንት ዘወረደ፣ ሁለተኛው ሳምንት ቅድስት፣ ሦስተኛው ሳምንት ምኲራብ፣ አራተኛው ሳምንት መጻጉዕ፣ አምስተኛው ሳምንት ደብረ ዘይት፣ ስድስተኛው ሳምንት ገብር ኄር፣ ሰባተኛው ሳምንት ኒቆዲሞስ ሲሆን ስምንተኛውና የመጨረሻው ሳምንት ከትንሣኤ ቀድሞ የሚገኝ የሕማማት መግቢያ ዋዜማ ላይ የሚከበረው ከዘጠኙ አበይት በዓላት መካከል አንዱ የሆነው በዓለ ሆሣዕና ነው፡፡

ይህ የሆሣዕና በዓል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርባ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ የሚቀድሙት እና የሚከተሉት ህዝብ በተለይም አእሩግ እና ሕጻናት “ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም ሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም” በማለት ጌታችንን መቀበላቸው የሚታወስበት በዓል ነው።

በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ የሆሣዕና በዓል ከረቡዕ ጀምሮ የሚታሰብ ታላቅ የቤተ ክርስቲያን በዓል እንደ ሆነና በዕለተ እሑድ ከቅዳሜ ምሽት ጀምሮ በደማቅ ሥነ ሥርዓት እንደሚከበር ይታወቃል። በዚሁ በዓለ ሰንበትና ከዋዜማው በፊት በነበሩት ዕለታት/ጥቂት ቀናት/ የሚዘመረው ጾመ ድጓ ‘ሆሣዕና በአርያም፣ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት፣ዕለተ ሆሣዕናሁ አርአየ፣… ወዘተ. የሚለው የቅዱስ ያሬድ ቀለም ይባላል፡፡

በዚህ ዕለት ሆሣዕና የሚለውን ቃል ቅዱስ ያሬድና ሌሎችም አባቶች በቅዱሳት መጻሕፍት የጠቀሱት እየተወሳ እየተዘመረለት በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ኢየሩሳሌም የገባበትን ሁኔታ እየተተረከ ስለሚዘመር ልዩ የምስጋና ቀን ነው፡፡

ይህ የሆሣዕና ሰንበት በጌትነትና በክብር በውዳሴና በዝማሬ ሆሣዕና በአርአያም እየተባለ በሽማግሌዎችና በሕፃናት አንደበት በድንጋዮችም ልሳን ሳይቀር እየተመሰገነ ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በከብር ሲገባ በምስጋና ለተባበሩት ሁሉ ለሰጣቸው ለተቀደሰ ሰላሙና ፍቅሩ መታሰቢያ ሆኖ የሚከበር ቀን ነው።

አስቀድሞ በነቢየ እግዚአብሔር ዘካርያስ እንደተነገረው ‘አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ እጅግ ደስ ይበለሽ ፣አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ እልል በይ እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው ትሑትም ሆኖ በአህያም በአህያያቱም ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል’’ ይላልና ይህንን የትንቢት ቃል ፈጸመው ፡፡ (ዘካ.፱፥፱)

ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይድረሰውና አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ነቢያትን ትንቢት ሳያናግር፣ለአበው በምሳሌ እና በራእይ ሳይገለጥ የፈጸመው የማዳን ሥራ እንደሌለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ብሉይን ከሐዲስ አስማምታ በሊቃውንቱ ትርጓሜ አመሥጥራ ታስተምራለች፡፡ በዕለተ ሆሣዕናም የሆነው ሁሉ ከላይ እንዳየነው ቀድሞ በትንቢተ ነቢያት የተነገረ፣በቅዱሳን አበው በምሳሌ የተገለጠ ሲሆን ፍጻሜውን አግኝቷል፡፡ ይህም አራቱም ወንጌላውያን ተባብረው የጻፉት ሲሆን እስኪ ወንጌላዊው ማቴዎስ የጻፈውን እንመልከት፡-

“ጌታችን ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም ቀርቦ ወደ ደብረ ዘይት ወደ ቤተ ፋጌ በደረሰ ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱን ላከ እንዲህም አላቸው በፊታችሁ ወደ አለችው መንደር ሂዱ ያንጊዜም የታሰረች አህያ ከውርንጫዋ ጋር ታገኛላችሁ ፍቱና አምጡልኝ “ምን ታደርጋላችሁ የሚላችሁ ቢኖር ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ ያን ጊዜ ይሰዱአችኋል” ይህም ሁሉ የሆነው በነቢይ እንዲህ ተብሎ የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ነው… ደቀ መዛሙርቱም ሄደው ጌታችን ኢየሱስ እንደ አዘዛቸው አደረጉ አህያይቱንና ውርንጫዋንም አመጡለት ልብሳቸውንም በላያቸው ጫኑ ጌታችን ኢየሱስም በእነርሱ ላይ ተቀመጠ ብዙ ሕዝብም ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ ሌሎችም ከዛፎች ጫፍ ጫፉን እየቆረጡ በመንገድ ላይ ያነጥፉ ነበር”(ማቴ.፳፩፥፩ ) ፡፡

በዚህ ገጸ ንባብ እንደተመለከትነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ   በቤተ ፋጌ መንደር ውስጥ ታስረው የነበሩ አህያቱንና ውርንጫዋን ፈትታችሁ አምጡልኝ በማለት በሞት ጥላ፣ በዲያብሎስ ቁራኝነት፣ በሲኦል በርነት ታሥሮ ይሠቃይ የነበረውን የሰውን ልጅ ከባርነት ነፃ ለማውጣትና ከኃጢአት ማሠሪያ ለመፍታት የመጣ መሆኑን ሲያስረዳ “ፈታችሁ አምጡልኝ” አለ፡፡ ይኸውም ሰው ሁሉ ከኃጢአት ማሠሪያ የሚፈታበት ጊዜ እንደደረሰ ለማጠየቅ ሲሆን በደላችንን ሁሉ ይቅር ብሎ በምሕረቱ ጎብኝቶን በእኛ አድሮ ይኖር ዘንድ ሊቀድሰን በደሙ ፈሳሽነት ከኃጢአታችን ሊያነጻን መዋረዳችንን አይቶ ስለ እኛ እሱ ተገብቶ መከራ መስቀልን በመቀበል ወደ ቀድሞ ክብራችን ሊመልሰን እንደ መጣ ለማሳየት ነው፡፡

“ማንም ምንም ቢላችሁ ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ” ማለቱም የጠፋናውን እኛን ሁላችንን ሊፈልግ የመጣ በመሆኑ በኃጢአት ማሠሪያ ለተያዝን ሁሉ ነጻነትን ሰጥቶ ልጆቹ ሊያደርገን መምጣቱን ሲነግራቸው የታሠረችውን አህያ ከነ ውርንጭላዋ ፈታችሁ አምጡልኝ አለ፡፡

በዚያችም ዕለት ክብር ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚሳነው ነገር የለምና በአህያዋና በውርንጭላዋ ላይ በተአምራት በአንድ ጊዜ ተቀምጦባቸዋል፡፡  ብዙዎችም ልብሳቸውን በአህያዋና በውርንጫዋ ላይ አነጠፉ በመንገዱም ላይ እየተሸቀዳደሙ የለበሱትን ልብስ ሳይቀር አነጠፉላቸው ይህንንም ያደረጉት መንፈስ ቅዱስ ምሥጢር እያስተረጎማቸው መሆኑን እንረዳለን፡፡  ይኸውም በአህያዋ ጀርባ ኮርቻ ከማድረግ ይልቅ ልብሳቸውን ማንጠፋቸው ኮርቻ ይቆረቁራል ልብስ አይቆረቁርም የማትቆረቁር ሕግ ሠራህልን ሲሉ፤ አንድም ልብስ በአካል ያለውን ነውር ይሸፍናል አንተም ከባቴ አበሳ /በደልን የምትሸፍን/ ነህ ሲሉ ነው፡፡

በአህያ የተቀመጠበት ምክንያት ደግሞ ቀድሞ ነቢያት  የጦርነት፣የበሽታ፣የረኃብ ዘመን የሚመጣ እንደሆነ  በፈረስ ተቀምጠው ይታያሉ፡፡ ዘመነ ሰላም የሆነ እንደሆነ በአህያ ተቀምጠው መነሳንስ ይዘው ይታያሉና ዘመነ ሰላም ደረሰ ሲል ትንቢቱን ባወቀ  አናግሯል፡፡ ምስጢሩም በአህያ የተቀመጠ ሸሽቶ  አያመልጥም አሳዶም አይዝም እሱም ካልፈለጉኝ አልገኝም ከፈለጉኝም አልታጣም ሲል ነው፡፡ ሲሄዱም ሕዝቡ ልብሳቸውን በመንገድ ማንጠፋቸው አንተ የተቀመጥክባት አህያ መሬት መርገጥ አይገባትም ሲሉ ነው፡፡

እንዲሁም ሕዝቡ፣ ሕፃናቱ ሳይቀሩ ዘንባባ ይዘው የሚቀድሙትም የሚከተሉትም “ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት፣ ቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ለዳዊት ልጅ መድኃኒትን መባል ይገባዋል፣ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፡፡ ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ያመሰግኑ ነበር፡፡ ታላላቆችም ሆኑ ታናናሾች የሰላም አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ላይ ተቀምጦ ሲሄድ ዘንባባ ይዘው አመስግነውታል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ሲያመሰግኑ ከሕዝቡ መካከል ከፈሪሳውያንም “መምህር ሆይ ደቀ መዛሙርትህን ገሥጻቸው አሉት፡፡ መልሶም እላችኋለሁ እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ያመሰግናሉ አላቸው” ይህም እንደሚቻል በግልጽ ድንጋዮች ሳይቀሩ አመስግነውታል፡፡ (ሉቃ. ፲፱፥፵)

በመሆኑም የሆሣዕና በዓል በቤተክርስቲያን ጌታ ወደ ቤተመቅደስ ሲገባ ሕዝቡ ፀበርት ወይም ዘንባባ በመያዝ “ቡርክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረክ ነው”  በማለት ስለተቀበሉት ይህን በማሰብና በማድረግ ቤተክርስቲያናችን ዘንባባ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ታድላለች።(መዝ.፻፲፯፥፳፮) በቤተክርስቲያን በአራቱም ማዕዘናት ይህን በዓል የሚመለከቱ ምንባባት ይነበባሉ፡፡ ሥርዓቱም ከሌሎች ቀናት ለየት በሚል መልኩ ይከናወናል፡፡ እነዚህም (ማቴ.፳፩፥፩-፲፯፣ ማር.፲፩፥፩-፲፣ሉቃ.፲፱፥፳፱፣ ዮሐ.፲፪፥፲፪) በየማዕዘኑ የሚነበቡ  ምንባባት ናቸው፡፡

በዚህ  መሠረት ዕለቱ የምስጋና ቀን እንደመሆኑ ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ጀምሮ ልዩ ድባብ ባለው ሥርዓት ዘንባባ በመያዝ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ ምእመናን ሁሉ ያሉበት የጸሎትና የምስጋና ሥርዓት ይከናወናል፡፡ ከላይ እንደ ተመለከትነው ሕፃናትና አረጋውያን  በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት “ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ፣ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተመሰገነ ነው” እያሉ ሲዘምሩ  አይሁድ በቅንዓት ስለተናደዱ የምስጋና ማዕበል ያቀርቡ የነበሩትን ሕፃናትን መከልከልና ዝም እንዲሉ መገሠጽ ሞከሩ፡፡

እነሱ ግን ከአይሁድ ቁጣ ይልቅ ለኢየሱስ ክርስቶስ በሚያቀርቡት ምስጋና ደስ ተሰኝተው ይበልጥ ድምጻቸውን ከፍ እያደረጉ “ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት” እያሉ አመሰገኑት፡፡ አይሁድም ኢየሱስ ክርስቶስን “ዝም እንዲሉ ገሥጻቸው” አሉት፡፡ እሱ ግን ሕፃናቱ እንዲዘምሩ በሚያበረታታ ቃል እንዲህ ሲል መለሰላቸው “አስቀድሞ በነቢይ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ” እንደተባለ አታውቁምን እናንተ እንዳሰባችሁት ሕፃናቱ ዝም ቢሉ እንኳን እነዚህ ድንጋዮች ያመሰግኑኛል” አላቸው፡፡(መዝ.፰፥፪) ያን ጊዜም የቢታንያ ድንጋዮች በሰው አንደበት በተአምር አመስግነውታል፡፡

ፍጥረት ሁሉ እንዲያመሰግነው ማድረግ ይቻለዋልና በቢታንያ ድንጋዮች ተመሰገነ፡፡  ስለ ሁሉ ነገር በየትኛውም ጊዜና ሁኔታ ውስጥ ብንሆን ፈጣሪያችንን  ማመስገን  አለብን፡፡ የተፈጠርነውም ስሙን ለመቀደስ ክብሩን ለመውረስ ነውና፡፡ ስሙን ለመቀደስ ማለት ስሙን ለማመስገን ማለት ሲሆን  ክብሩን ለመውረስ ማለት ደግሞ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ማለት ነው፡፡ የተፈጠርነው ለዚህ የተቀደሰ ዓላማ ስለሆነ ሁል ጊዜ እግዚአብሔርን ማመስገን ይገባል፡፡ ምስጋናውም በፍጽም እምነት፣ በቅንነትና በንጹሕ  ልብ  መሆን  አለበት፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት “እባርኮ  ለእግዚአብሔር  በኵሎ  ጊዜ  ወዘልፈ  ስብሐቲሁ  ውስተ  አፉየ፤ እግዚአብሔርን ሁልጊዜ አመሰግነዋለሁ ምስጋነውም ዘወትር በአፌ ነው” በማለት እንደተቀኘ እኛም ሁል ጊዜ እግዚአብሔርን ማመስገን የዘወትር ተግባራችን ሊሆን  ይገባል፡፡(መዝ.፴፫፥፩)

የቅዱሳን አምላክ ልዑል እግዚአብሔር ለምስጋና የነቃን የተጋን ያድርገን አሜን፡፡

“…ኒቆዲሞስ የተባለ አንድ ሰው ነበረ ”(ዮሐ.፫፥፩)

 በቀሲስ ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

የዐቢይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት ኒቆዲሞስ ይባላል፡፡ ይህም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሌሊት ወደ እርሱ እየመጣ ይማር ለነበረው  ኒቆዲሞስ ለተባለ ፈሪሳዊ ሰው የዳግም ልደትን ምሥጢር (ምሥጢረ ጥምቀትን) ያስተማረበት በመሆኑ ኒቆዲሞስ ተብሏል፡፡

ኒቆዲሞስ በሕይወት ዘመኑ ቅንናና መልካም ሰው እንደነበር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በቀን ለመገናኘት ሁኔታው ባይፈቅድለትም በሌሊት እየመጣ የሕይወት ቃል በመማር ያልገባውንም በመጠየቅ ያሳየው ቁርጠኝነት ምስክር ነው፡፡ በሌላም መልኩ ስንመለከተው የኒቆዲሞስ የብሉይ ኪዳን መምህርነቱ የአይሁድም አለቅነቱ እንደ ሌሎች ጸሐፍት ፈሪሳውያን በምቀኝነትና በራስ ወዳድነት የተሸፈነ ስላልነበረ የክርስቶስን አምላክነት ለመረዳት ጊዜ አልወሰደበትም፡፡ ምክንያቱም በወቅቱ የነበሩ የአይሁድ ሹማምንት በተለያዩ ምክንያቶች በክሕደት ማዕበል የተዋጡበት ጊዜ ስለ ነበረ ነው፡፡

በዚህ ወቅት አይሁድ በክፋትና በምቀኝነት ተጠምደው የኢየሱስ ክርስቶስን አዳኝነት ለመሸፈንና አማላክነቱን ላለመቀበል እንኳንስ በአለቅነት መዓርግ ያለውን ኒቆዲሞስን ይቅርና ተራውን ሰው እንኳን ክርስቶስን እንዳይከተሉ ተጽዕኖ ያደርሱባቸው ነበር፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደ ጻፈው ፈሪሳዊው ኒቆዲሞስ የአይሁድ ዛቻና ማስፈራሪያ ሳይበግረው የሌሊቱ ጨለማ ሳያስፈራው በሌሊት የኢየሱስ ክርስቶስን ትምህርት ይከታተል ነበር፡፡

ኒቆዲሞስ የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት የሚያሳዩ የማዳን ሥራዎቹን የቃሉን ትምህርት፣የእጁን ተአምራት አይተው ካመኑበት ሰዎች መካከል አንዱ ነው፡፡ ያልገባውን ጠይቆ በመረዳትም ጭምር ቅንነቱን እና የዋህነቱን አሳይቶአል፡፡ በተለይም ደግሞ ለጥያቄው መልስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሰጠው ትምህርቱ እስኪገባው ድረስ እንዴት፣ከየት፣መቼ፣ማን፣ እያለ በመጠየቅ እውነትን በመፈለግ የተጋ ብልህ ሰው ነው፡፡

ከትምህርት በኋላም ኢየሱስ ክርስቶስን በእግር ብቻ ሳሆን በልቡ አምኖ የተከተለ፡፡ ጌታችን ነፍሱን ከሥጋው በፈቃዱ አሳልፎ በሰጠም ጊዜ ሥጋውን ከመስቀል አውርደው የቀበሩት ዮሴፍና ይሄው መልካሙ ሰው ኒቆዲሞስ ናቸው፡፡ ለዚህም ነው በበዓለ ኀምሳ የቅዳሴ ሥርዓት ቀዳስያኑ ከቤተልሔም  ወደ ቤተ መቅደስ ሲገቡ  “ሃሌ ሉያ ዮሴፍ ወኒቆዲሞስ ገነዝዎ ለኢየሱስ በሰንዱናት ለዘተንሥኣ እሙታን በመንክር ኪን፤ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ድንቅ በሚሆን ጥበብ ከሙታን ተለይቶ የተነሣውን ኢየሱስን በበፍታ ገነዙት” የሚለውን የምስጋና ቃል በዜማ እያሰሙ የሚገቡት (ሥርዓተ ቅዳሴ ዘበዓለ ኀምሳ)፡፡

በመሆኑም ኒቆዲሞስ እስከ መጨረሻው ድረስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የተከተለ የቁርጥ ቀን ባለሙዋሉ ነው፡፡ እምነቱ ፍርሀቱን አርቆለት በጽናት ሆኖ የጌታችን ቅዱስ ሥጋ ከመስቀል አውርዶ በአዲስ መቃብር ገንዞ በክብር በመቃብር ለማኖር የተመረጠ ቅዱስ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድም  በምስጋናው ውስጥ ይህን መልካም ሰው በመዘከር  ለዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜን  ሲሰጥ ሰባተኛውን ሳምንት ኒቆዲሞስ በማለት በስሙ እንዲጠራ አድርጎአል፡፡ ኒቆዲሞስ አመጣጡ ከፈሪሳውያን ባለ ሥልጣናት ሲሆን ከማያምኑት የሚለይበትን እምነት ለማጽናት በጆርው የሰማውን እና በዐይኑ ያየውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የማዳን ሥራ  እየመሰከረ ያልገባውንም ቀርቦ በመጠየቅ እምነቱን ወደ ፍጹምነት አሳድጎታል፡፡ ለሚያነሣቸው ትያቄዎችም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የሚሰጡትን መልሶችና ማብራሪያዎችን በጥሙና ይሰማ ነበር፡፡ ጌታችንም በምሳሌ ጭምር እንዳስረዳው ወንጌላዊው  ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ ሲል በሰፊው ጽፎታል፡፡

“ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የተባለ አንድ ሰው ነበረ፡፡ እርሱም በሌሊት ወደ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ እንዲህ አለው “መምህር ሆይ ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ይህንን ተአምር ሊያደርግ የሚችል የለምና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እውነት እውነት እልሀለሁ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” አለው፡፡ (ዮሐ.፫፥፩ )

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ በምሳሌ ጭምር እንዳስተማረው የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ (ለመዳን) የልጅነት ጥምቀት የግድ አስፈላጊ ነው፡፡  በዚያው የወንጌል ክፍል ዝቅ ይልና  “ኒቆዲሞስም ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይችላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን? አለው ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፡፡ እውነት እውነት እልሀለሁ ዳግመኛ ከውሃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፤ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፤ከመንፈስ የተወለደ መንፈስ ነውና›› (ዮሐ.፫፥፬) በማለት አስረዳው፡፡

ጌታችን እንዳስተማረን የሰው ልጅ ዳግም ከውኃና ከመንፈስ ሲወለድ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ይሆናል፡፡ መንፈስ ቅዱስም ስለሚያድርበት የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ ለእግዚአብሔር የተለየ ዙፋን፣የእግዚብሔር ቤተ መቅደስ ይሆናል፡፡ በዘመነ አበውም ሆነ በዘመነ ኦሪት ራሳቸውን ከርኲሰትና ከኃጢአት ለይተው ለእግዚአብሔር ክብር ከተለዩ ምእመናን ጋር እግዚአብሔር በረድኤት ነበረ፡፡ በሐዲስ ኪዳን ግን ዳግም ስንወለድ የእግዚአብሔር ልጆች ስለምንሆን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያዎች ለመሆን እንሠራለን፡፡

ዳግም ልደት የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ለመሆንና የመንግሥቱ ወራሾች መሆን የምንችልበት ምሥጢር ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስም በመልእክቱ #እናንተ ግን ለመንፈሳዊ ሕግ እንጂ ለሥጋችሁ ፈቃድ የምትሠሩ አይደላችሁም፤የእግዚአብሔር መንፈስ በእናንተ አድሮ ይኖራልና፤የክርስቶስ መንፈስ ያላደረበት ግን እርሱ የእርሱ ወገን አይደለም፤ክርስቶስ ካደረባችሁ ግን ሰውነታችሁን ከኃጢአት ሥራ ለዩ፤መንፈሳችሁንም ለጽድቅ ሥራ ሕያው አድርጉ ጌታችን ኢየሱስን ከሙታን ለይቶ ያስነሣው የእግዚአብሔር መንፈስ ካደረባችሁ ኢየሱስ ክርስቶስን ከሙታን ለይቶ ያስነሣው እርሱ አድሮባችሁ ባለ መንፈሱ ለሟች ሰውነታችሁ ሕይወትን ይሰጣል$ (ሮሜ ፰፥፱) ይላል፡፡

ዳግም ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ የተወለደው የክርስቲያን አካል የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የመንፈስ ቅዱስ ቤት፣የመንፈስ ቅዱስ ዙፋን ነው፡፡ ይህንን አካል በንጽሕና በቅድስና መያዝ የሚያድርበትን እግዚአብሔርን ማክበር ነው፡፡ እግዚአብሔር ንጹሐ ባሕርይ ነውና ያድርበት ዘንድ ንጹሕ ነገርን ይወዳል፡፡ በኃጢአትና  በበደል  በተጐሳቆለ አካል  ላይ  እግዚአብሔር አያድርም፡፡ የእርሱ ማደሪያ፣ለመሆን በኃጢአት ያደፈውን ማንነት በንስሓ ማጠብና ማንጻት ያስፈልጋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች በላከላቸው መልእክቱ “ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር ለተቀበላችሁት በእናንተ አድሮ ላለ ለመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን? ለራሳችሁም አይደላችሁም በዋጋ ተገዝታችኋልና፤ስለዚህ እግዚአብሔርን በሥጋችሁ አክብሩ” (፩ኛቆሮ.፮፥፲፱) ይላልና፡፡

ሐዋርያው እንደገለጸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የተሰቀለውና ደሙን ያፈሰሰው በዲያብሎስ ግዛት ሥር ወድቆ የነበረውን፤ የሰው ልጅ ነጻ ለማውጣት ነው፡፡ በሲኦል የነፍስ መገዛትን፤ በመቃብር የሥጋን መበስበስ፣ አስወግዶ በፊቱ ሕያዋን አድርጎ ሊያቆመን

ስለ በደላችን የደሙን ዋጋ ከፍሎ ገዝቶናልና የራሳችን አይደለንም፡፡ በዋጋ የተገዛን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ቤተ መቅደስ ነን እንጂ፡፡

ይህንን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሆነ አካላችን በኃጢአት ብናቆሽሽ በዋጋ የተገዛ አካል ነውና ተጠያቂዎች ነን፡፡ “እናንተ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንደሆናችሁ የእግዚአብሔር መንፈስም በእናንተ ላይ አድሮ እንደሚኖር አታውቁምን? የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ የሚያፈርሰውን ግን እርሱን ደግሞ እግዚአብሔር ያፈርሰዋል፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነውና፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስም እናንተ ራሳችሁ ናችሁ እንግዲያስ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ አታርክሱ” (፩ኛቆሮ.፫፥፲፮)

በሐዲስ ኪዳን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወርቀ ደሙ ፈሳሽነት የዋጀን እያንዳንዳችን የእግዚአብሔር ማደሪያ ቤተ መቅደስ፣ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ነን፡፡ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መሆን እጅግ የከበረ ማንነት ነው፡፡ ይህም የሚያሳየው እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ምን ያህል እንዳከበረውና እንደወደደው ነው፡፡ ለሰው ልጅ ወደር የሌለው ፍቅሩን የገለጠበትም ታላቅ ምሥጢር ነው፡፡ እግዚአብሔርን ያህል በባሕርዩ ቅዱስ የሆነ ጌታ በእኛ በደካሞችና በበደለኞች አካል ማደሩ እጅግ የሚያስደንቅ ቸርነት ነው፡፡ ይህንን ስንረዳ እግዚአብሔር ለእኛ ያደረገውን ምሕረት እናደንቃለን፡፡

በወንጌል እንደ ተጻፈው በእርሱ ሕይወት ይሆንልን ዘንድ የሚወደውን አንድያ ልጁን ወደ ጎስቋላዋ ዓለም ልኮታል፡፡ “በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲያገኝ እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ቤዛ አድርጎ እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲህ ወዶታልና” እንዲል፡፡ (ዮሐ.፫፥፲፮)

እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍጹም ፍቅሩን ማስተዋል ከቻልን  የመንፈስ  ቅዱስ  ቤተ  መቅደስ  የሆነ  አካላችንን  የኃጢአት  መሣሪያ  ለማድረግ አንደፍርም፡፡ ምክንያቱም ቀደም ብለን እንዳየነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “በዋጋ ተገዝታችኋልና የራሳችሁ አይደላችሁም” በማለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዋጋ የገዛን ገንዘቡ እንደሆንን አስገንዝቦናል፡፡ ይኸው ሐዋርያ “ሥጋችሁ የክርስቶስ አካል እንደሆነ አታውቁምን? እንግዲህ የክርስቶስን አካል ወስዳችሁ የአመንዝራ አካል ታደርጉታላችሁን?   አይገባም››ይላልና፡፡ (፩ኛቆሮ.፮፥፲፭)

በክርስቶስ ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ መንፈሳዊ የተሰኘን መሆናችንን ሁልጊዜም እያሰብን ሥጋዊ ፈቃድ ሳያሸንፈን ከኃጢአት ሥራ መራቅ ይኖርብናል፡፡ በኛ የሆኑ ሕዋሳቶቻችንን ሁሉ በማስተዋል መጠበቅና መቆጣጠር በተለይም ወጣቶች ያለንበት የዕድሜ ክልል በራሱ ፈታኝ መሆኑን ተረድተን ለስሜታችን ሳይሆን  ለሕገ እግዚአብሔር መገዛት እንደሚገባን ላፍታም መዘንጋት የለብንም፡፡ እንደ ኒቆዲሞስ ያልገባንን ወደ አባቶቻችን ካህናት እየቀረብን በመማርና በመጠየቅ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን መትጋት ይጠበቅብናል፡፡

             የእግዚአብሐር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን:: ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም ያድርሰን አሜን፡፡

የኒቆዲሞስ መንፈሳዊ ዕድገት

ኤልያስ ገ/ሥላሴ

አሐቲ፣ ቅድስት፣ ኵላዊት እና ሐዋርያዊት የሆነችው ቤተክርስቲያናችን እኛ ምእመኖቿ በዓለም ሐሳብ ድል እንዳንነሣ፣ ይልቅስ ፍትወታትን ሁሉ ድል አድርገን ራሳችንን ገዝተን (ተቈጣጥረን) በውስጣችን ፈቃደ እግዚአብሔርን አንግሠን ምድራዊውን ሳይሆን ሰማያዊውን እያሰብን እንድንኖር በዓመቱ ውስጥ በተለያዩ ወራት የሚጾሙ አጽዋማትን ሠርታልናለች፡፡ ከነዚህ አጽዋማት ውስጥ አንዱና ዋነኛው ደግሞ አሁን በዚህ ወቅት እየጾምነው ያለነው ዐቢይ ጾም ነው፡፡ ዐቢይ ጾም የኀምሳ አምስት ቀን ጾም ሲሆን፣ በውስጡም ስምንት ሳምንታት አሉ፡፡ እነዚህ ስምንት ሳምንታት ሁሉም የየራሳቸው መጠሪያ ስም ሲኖራቸው ሰባተኛው ሳምንት ኒቆዲሞስ በመባል ይታወቃል፡፡

ይህ ሰባተኛ ሳምንት ታሪኩን በዮሐንስ ወንጌል ምዕ.፫፤፩ ጀምሮ በምናገኘው በኒቆዲሞስ ስም የተሰየመ በመሆኑ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገን ሲሆን የእስራኤል መምህርና የአይሁድ ሸንጎ አባል ነበር፡፡ የስሙ ትርጓሜም “የሕዝብ ገዢ” እንደ ማለት ሲሆን፣ በትውፊት እንደሚታወቀው ኒቆዲሞስ በአይሁድ ላይ አለቃ ከመሆኑ በተጨማሪ እጅግ ባለጸጋም ነበር፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፋሲካ በዓል በኢየሩሳሌም ሳለ ያደረገውን ተአምራት አይተው ብዙዎች አምነውበት ነበር፡፡ ኒቆዲሞስም ከነዚህ ምልክትን አይተው ካመኑ አማኞች ውስጥ አንዱ ነው፡፡ (ዮሐ.፪፥፳፫)፡፡ ኒቆዲሞስ በሌሊት ወደ ኢየሱስ ሄዶ “መምህር ሆይ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን” እንዳለውም ተጽፏል፡፡ (ዮሐ.፫፡፪)፡፡ ይሁንና ኒቆዲሞስ የኦሪት ሊቅ እንደመሆኑ መጠን በብሉይ ኪዳን ዘመን እግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር በመሆኑ ምክንያት ታላላቅ ድንቆችንና ምልክቶችን ሲያደርጉ ስለነበሩ ነቢያት ያውቅ ነበርና ኢየሱስ ክርስቶስም እንደ ሙሴና ኢያሱ ሁሉ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ስለሆነ ድንቆችን የሚያደርግ እንደሆነ እንጂ ራሱ እግዚአብሔር እንደሆነ አላወቀም ነበር፡፡ (ዘፍ.፳፮፥፳፬፤ኢያ.፩፥፭)

ኒቆዲሞስ በሌሊት ወደ ጌታ መምጣቱ (ዮሐ.፫)

ኒቆዲሞስ በመጀመሪያ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጣው በቀን ሳይሆን በሌሊት ነበር፡፡ ለዚህም የቤተ ክርሰቲያን አባቶች በዋናነት ሁለት ምክንያቶችን ያስቀምጣሉ፡፡ የመጀመርያው የአይሁድ መምህር ሆኖ ሳለ በቀን በሕዝብ ፊት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መማር ስላፈረ ነው የሚል ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ አይሁድ “ከእኛ ወገን በክርስቶስ ያመነ ቢኖር ከምኩራብ ይሰደድ” የሚል አዋጅ አውጀው ነበርና ያንን ፈርቶ ነው ይላሉ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ፍራቻዎች ኒቆዲሞስን ወደ ክርስቶስ ከመምጣት አላገዱትም፡፡

ኒቆዲሞስ በርቀት በአደባባይ ድንቅ ተአምራትን ሲያደርግ ያየውን ኢየሱስ ክርስቶስን  ቀርቦ መጠየቅ ፈልጓል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካደረጋቸው ተአምራት የተረዳው ነገር ቢኖርም ቀርቦ ደግሞ ከእርሱ ከራሱ ስለማንነቱ መስማት ፈልጓል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ በኒቆዲሞስ እይታ እግዚአብሔር አብሯቸው እንደነበረ እንደቀደሙት የእስራኤል አባቶች መስሎት ነበር፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አብሮት ካለ ሰው በስተቀር እርሱ የሚያደርጋቸውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና፡፡ ወደ ክርስቶስ ቀርቦም ያለው ይህንኑ ነው፡፡ “መምህር ሆይ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን” አለ፡፡

ኒቆዲሞስ መጀመሪያ ወደ ክርስቶስ ሲመጣ ልክ እንደ ናትናኤል “መምህር ሆይ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ” (ዮሐ.፩፥፶) ብሎ አምላክነቱን አምኖና መስክሮ አልነበረም፡፡ በኒቆዲሞስ እይታ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእግዚአብሔር ተልኮ የመጣ መምህር መሰለው እንጂ አምላክነቱን አልተረዳም ነበር፡፡ የክርስቶስ አምላክነት እና የዓለም መድኃኒትነት ገና አልተገለጠለትም፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ይህንን ስላወቀ ለኒቆዲሞስ የሚድንበትን እና ስለ እርሱ ማንነት የሚያውቅበትን ትምህርት አስተምሮታል(ዮሐ.፫፥፲፫)፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ያስተማረውን ሲያብራራ “ሰው ከውኃና ከመንፈስ ድጋሜ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ማየት አይችልም፡፡ አንተ ገና ከእግዚአብሔር አልተወለድክምና ስለ እኔ ያለህ ዕውቀት መንፈሳዊ ሳይሆን ሥጋዊና ሰዋዊ ነው፤ ግን እልሃለሁ ማንም ሰው ከእግዚአብሔር ድጋሚ ካልተወለደ በስተቀር ክብሬን ማየት አይችልም ከመንግሥቴም ውጪ ነው” እንዳለ፡፡

ኒቆዲሞስ ፈሪሳዊ ነው፡፡ ፈሪሳውያን ደግሞ የአብርሃም ልጆች በመሆናቸው እጅግ የሚመኩና ዳግም ስለመወለድ ቢነገራቸው ፈጽመው የማይቀበሉ ነበሩ (ዮሐ.፰፥፴፫)፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ምንም ስንኳ ከፈሪሳውያን ወገን ቢሆንም ክርስቶስ ዳግም መወለድ እንዳለበት ሲነግረውና የአይሁድ መምህር ሆኖ ሳለ ክርስቶስ እየነገረው ያለውን ነገር ባለመረዳቱ ምክንያት “አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ፣ ነገር ግን ይህን እንዴት አታውቅም?” ብሎ ሲገሥጸው በእምነት ተቀብሎ ተጨማሪ ጥያቄ ወደ መጠየቅ አለፈ እንጂ “የአብርሃም ዘር ሆኜ ሳለ እንዴት ድጋሚ መወለድ አለብህ ትለኛለህ?” አላለም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የአይሁድ መምህር ሆኖ ሳለ ምንም ስንኳ በቀን በሰዎች ፊት ሊያደርገው ባይደፍርም የራሱን ኩራት (ትዕቢት) አሸንፎ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጠይቆ ለመማር ወደኋላ አላለም፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ይህን ፍላጎቱ በማየት ታላቁን ምሥጢር አስተምሮታል፡፡ “ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣንን ሰጣቸው” (ዮሐ.፩፥፲፪)ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ ይህ ልጅነት እንዴት እንደሚሰጥ በግልጥ የተነገረውም ለኒቆዲሞስ ነው (ዮሐ፫፥፭)፡፡ ይህን ታላቅ ምሥጢር የገለጸለትም ስለ ትሕትናውና ራሱን ዝቅ ስለ ማድረጉ ነው፡፡

ሰው በማንነቱና ባለው ነገር ለራሱ ከፍተኛ ግምት ሲኖረው በትዕቢት ኃጢአት ይወድቃል፡፡ ሰው በሀብቱ፣ በሥልጣኑ፣ በዘሩ፣ በዘመዶቹ፣ በዕውቀቱ፣ በመልኩ …ወዘተ ምክንያት የትዕቢት ስሜት ሊያድርበት ይችላል፡፡ ክርስቲያን የሆነ ሰው ግን እነዚህ ሁሉ አላፊና ጠፊ መሆናቸውን አውቆ ትምክህቱን ሊያድኑት ከማይችሉ ምድራዊ ነገሮች ላይ አንሥቶ በእግዚአብሔር ላይ ማድረግ አለበት(መዝ.፻፵፭፥፫፤ መዝ ፫፥፰)፡፡ ከነዚህም በተጨማሪ ትዕቢት በትሩፋት ሕይወት ላይ ያሉትን ሳይቀር ሊያጠምድ ይችላል፡፡ የሚጾመው ከማይጾመው፣ የሚጸልየው ከማይጸልየው፣ የሚያስቀድሰው ከማያስቀድሰው፣ የሚመጸውተው ከማይመጸውተው፣ ትሑቱ ከትዕቢተኛው፣ መነኩሴው ከሕጋዊው፣ ገዳማዊው ከዓለማዊው፣ ክርስቲያኑ ከአሕዛቡ … ወዘተ እሻላለሁ በሚል የትዕቢት ስሜት እንዳይወድቅ መጠንቀቅ አለበት፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሳቸውን ለሚያመጻድቁና ባልንጀራቸውን ለሚንቁ እንዲህ ብሎ መለሰላቸው “ሁለት ሰዎች ሊጸልዩ ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ አንዱ ፈሪሳዊ ሁለተኛውም ቀራጭ ነበር፡፡ ፈሪሳዊውም ቆመና እንዲህ ብሎ ጸለየ “አቤቱ እንደ ሌሎች ሰዎች እንደ ቀማኞችና እንደ ዐመፀኞች እንደ አመንዝሮችም ወይም እንደዚህ ቀራጭ ያላደረግከኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ እኔ በየሳምንቱ ሁለት ቀን እጾማለሁ፣ ከማገኘውም ሁሉ ከዐሥር አንድ እሰጣለሁ፡፡” ቀራጩ ግን ራቅ ብሎ ቆመ፤ ዓይኖቹንም ወደ ላይ ወደ ሰማይ ሊያነሣ አልወደደም፤ ደረቱን እየመታ “አቤቱ እኔን ኃጢአተኛውን ይቅር በለኝ” አለ፡፡ እላችኋለሁ ከዚያኛው ይልቅ ይህ ጻድቅ ሆኖ ወደ ቤቱ ተመለሰ፡፡ ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና፤ ራሱንም የሚያዋርድ ይከብራልና፡፡”(ሉቃ.፲፰፥፲-፲፬)፡፡ ስለዚህ ትዕቢት ወደ ኃጢአት የማይቀይረው ምንም ትሩፋት እንደሌለ ማስተዋልና እርምጃችንን ሁሉ በጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

ኒቆዲሞስ ባለ ሀብት፣ የአይሁድ መምህር እና አለቃ ሆኖ ሳለ በትዕቢት ሳይያዝ ራሱን በመንፈስ ድኃ አድርጎ ስለቀረበ “በመንፈስ ድኆች የሆኑ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና” በሚለው ቃል መሠረት መንግሥተ ሰማያትን ገንዘብ ማድረግ የሚችልበትን ትምህርት እንዲማር ሆኗል ምሥጢሩንም ገልጾለታል፡፡(ማቴ ፭፥፫)፡፡

ዳግም መወለድ ማለት ሥጋዊ፣ ምድራዊና ጊዜያዊ የሆነውን የድሮ ማንነታችንን ትተን  መንፈሳዊ፣ ሰማያዊና ዘለዓለማዊ የሆነውን አዲስ ማንነት ገንዘብ ማድረግ ማለት ነው፡፡ ይህ አዲስ ማንነትም ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ከመወለድ የሚገኝ ነው፡፡ ያጣነውንና የተወሰደብንን ጸጋ እርሱም የእግዚአብሔር ልጅነት የምናገኘው በጥምቀት ነው፡፡ “ጌታችን ከመንፈስ ቅዱስ እንድንወለድ ያዘዘን ሥጋዊው ልደት በሥጋ የወለዱንን የእናት የአባታችንን ርስት ያወርሰናል እንጂ ሰማያዊውን ርስት ሊያወርሰን አይችልምና ነው፡፡ ሰማያዊውን ርስት ልንወርስ የምንችለው መንፈሳዊውን ልደት ስንወለድ ነው፡፡ “እንኪያስ እናንተ ልጆች ናችሁ እንጂ ባሮች አይደላችሁም፤ ልጆች ከሆናችሁም በኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሾች ናችሁ፡፡” (ገላ ፬፥፯) እንዲል፡፡ መንፈሳዊውን ልደት የምንወለድ ደግሞ ከመንፈስ ቅዱስ ስለሆነ ዳግመኛ ከውሃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም በማለት አስተማረው፡፡

ጥምቀት ዳግመኛ ተወልደን ክርስቶስን የምንመስልበት ነው፡፡ “እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እኔን ምሰሉ” (1፩ኛቆሮ.፲፩፥፩) እንዳለ ሐዋርያው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ይህንን ለኒቆዲሞስ ሲያብራራ “ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው” እንዳለ ከሥጋ የተወለደ ሥጋን እንደሚመስል ከመንፈስ ቅዱስ የተወለደም መንፈስ ቅዱስን ይመስላልና፡፡(ዮሐ.፫፥፮)

ኒቆዲሞስ ስለ ጌታ ከአይሁድ ጋር መከራከሩ (ዮሐ.፯)

ኒቆዲሞስ ጌታ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት ላይ ያስተማረውን ትምህርት ተቀብሎና አምኖ ሄዷል፡፡ ለዚህም ሁለት ማሳያዎችን ማቅረብ ይቻላል፡፡ የመጀመርያው የወንጌላቱ ጸሓፍያን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰዎች ጋር ያደረገውን ንግግር ሲጽፉ ሰዎቹ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትምህርት የተቀበሉት እንደሆነ በዝምታ ያልፉታል፣ ያልተቀበሉት እንደሆነ ግን ይጽፉታል፡፡ ለምሳሌ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን “የዘላለም ሕይወት እንዳገኝ ምን መልካም ነገር ላድርግ” ብሎ የጠየቀው ሰው የክርስቶስን መልስ ከሰማ በኋላ አለመቀበሉ ተጽፏል፡፡ (ማቴ.፲፱፥፳፪፣ማር.፲፥፳፪፣ሉቃ ፲፰፥፳፫)፡፡ የኒቆዲሞስ ግን በዝምታ መታለፉ ትምህርቱን አምኖ ለመቀበሉ ማሳያ ነው፡፡ ሁለተኛው በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፯ ላይ የምናገኘው ኒቆዲሞስ በአይሁድ ፊት ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መከራከሩ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስና በትምህርቱ ለማመኑ ማሳያ ነው፡፡

ፈሪሳውያንና የካህናት አለቆች ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሊይዙት ሎሌዎችን ልከው ነበር፡፡ ሎሌዎቹ ግን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሳይዙት ተመለሱ፡፡ የካህናት አለቆቹና ፈሪሳውያኑ በዚህ ተቈጥተው ሲገሥጹአቸው ኒቆዲሞስ ጣልቃ ገብቶ ለእውነት ቆመ፡፡ “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” ብሎ ጠየቃቸው፡፡ ያ አይሁድን በመፍራቱ ምክንያት ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀን መሄድ ፈርቶ የነበረው ኒቆዲሞስ ጥላቻቸው እጅግ ከመጠን ያለፈ በመሆኑ ሕግ ጥሰው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሊይዙት የሚሹትንአይሁድ በግልጽ በአደባባይ ተቃወማቸው፡፡ ያን ጊዜ እምነቱ ጠንካራ ባልነበረ ጊዜ በድብቅ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሄደው ኒቆዲሞስ አሁን ግን ላመነበት ጌታ እና ለእውነት በአደባባይ ጥብቅና ቆመ፡፡

በፍርሃት፣ በዝምድና፣ በእውቅና፣ በገንዘብ …ወዘተ ምክንያት ከእውነት ይልቅ ለሐሰት ለምንቆም፣ ለባለ ጊዜዎች በማድላት ፍርድን ለምናጣምም ይህ ጥሩ ትምህርት ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ክርስቶስን ከሚከተሉት ከሐዋርያት ወገን አልነበረም፡፡ ቅርበቱ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ይልቅ ወገኖቹ ለነበሩት አይሁድ ነበር፡፡ ነገር ግን ኒቆዲሞስ በሐሰት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሊከሱት ለሚሹት ለወገኖቹ ለአይሁድ ሳይሆን ለእውነተኛው ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥብቅና ቆመ፡፡ ክርስቲያንም በጠባዩ እንዲህ መሆን አለበት፡፡ ሥጋ ላይ ብቻ ሥልጣን ያላቸውን ሳይሆንበሥጋም በነፍስምላይ ሥልጣን ያለውን አምላክ መፍራት አለብን፡፡ እውነት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ስለ እውነት መከራ የሚደርስበትና የሚሰደድ ደግሞ በወንጌል እንደተጻፈ ዋጋውን አያጣምና (ማቴ ፭፥፲፩-፲፪፡፡) ጊዜያዊውን መገፋት እየታገሥን ተድላ መንግሥተ ሰማያትን እያሰብን በጽናት መጓዝ አለብን፡፡

ኒቆዲሞስ በጌታችን ስቅለት ጊዜ (ዮሐ.፲፱)

ጌታችን በመስቀል ላይ ነፍሱን በገዛ ፈቃዱ አሳልፎ ከሰጠ በኋላ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ በአዲስ መቃብር ከቀበሩት ሁለት ሰዎች ውስጥ አንዱ ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም ይህንን ሲመሰክር “ደግሞም አስቀድሞ በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ የነበረ ኒቆዲሞስ መቶ ልጥር የሚያህል የከርቤና የእሬት ቅልቅል ይዞ መጣ የኢየሱስንም ሥጋ ወስደው እንደ አይሁድ አገናነዝ ልማድ ከሽቱ ጋር በተልባ እግር ልብስ ገነዙት፡፡ በተሰቀለበት ስፍራ አትክልት ነበረ በአትክልቱም ማንም ገና ያልተቀበረበት አዲስ መቃብር ነበረ፡፡ “ጌታችን ኢየሱስንም በዚያ ቀበሩት፡፡ ለአይሁድ የመሰናዳት ቀን ነበርና መቀብሩንም ለሰቀሉበት ቦታ ቅርብ ነበር፡፡” ብሏል፡፡

ኒቆዲሞስ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ  ክርስቶስ በድብቅ ከመምጣት በአደባባይ ለጌታችን  ለኢየሱስ ክርስቶስ እስከመመስከርና በኋላም ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ሙሉ ያስተማራቸው ደቀመዛሙርቱ(ከወንጌላዊው ዮሐንስ በስተቀር) ከፍርሃት የተነሣ ጥለውት በሸሹ ጊዜ እንኳ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ ለመቅበር እስከ መብቃት ደረሰ፡፡ በትውፊት እንደሚታወቀውም ኒቆዲሞስ ከቅዱስ ጴጥሮስና ከቅዱስ ዮሐንስ እጅ የክርስትና ጥምቀትን በመጠመቅስለ ክርስቶስ ስደትን የተቀበለ ጠንካራ ክርስቲያን እስከመሆን ደርሷል፡፡ ሉችያንየተባለ የኢየሩሳሌም ቄስ “የቅዱስ እስጢፋኖስ ቀዳሜ ሰማዕት ዐፅም መገኘት” በሚለው ጽሑፉ የቅዱስ ጳውሎስ የኦሪት መምህር የነበረው ገማልያል ተገልጦ ነገረኝ ብሎ ተከታዩን አስፍሯል፡፡ “አይሁድ ኒቆዲሞስ ክርስቲያን መሆኑን ሲያውቁ ከአለቅነቱ አንሥተው፣ ንብረቱን ሁሉ ቀምተውና ክፉኛ ደብድበው ሞቷል ብለው ትተውት ሄዱ፡፡ እኔ ገማልያል በመንገድ ከወደቀበት አንሥቼ ወደቤቴ ወሰድኩት፤ እስኪሞትም ድረስ ከእኔ ጋር ኖረ፡፡ በሞተም ጊዜ ከቅዱስ እስጢፋኖስ ቀዳሜ ሰማዕት አጠገብ ቀበርኩት” ብሏል፡፡ የኒቆዲሞስ ዐፅሙም በ፬፻፳፰ ዓ.ም ከኢየሩሳሌም ወደ ቁስጥንጥንያ ፈልሶ እስከአሁን ድረስ “ቅዱስ ዲያቆን ላውረንስ” በሚሉት ቤተክርስቲያን አለ፡፡

በወንጌልና በትውፊት ከሚታወቀው የኒቆዲሞስ ታሪክ የመንፈሳዊ ሕይወት ዕድገቱን በማስተዋል እኛም የክርስትና ጉዞአችን ምን እንደሚመስል መመልከት ይገባናል፡፡ ክርስትና ጉዞ ነው፡፡ ዕለት ዕለት በእምነት እየጠነከርን በትሩፋት እየበረታን እስከ ዕለተ ሞታችን ድረስ በጽናት መቆየት ያስፈልጋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር