የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት ክለሳ የግብአት ማሰባሰቢያ የውይይት መርሐ ግብር ተካሄደ

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ነባሩን ሥርዓተ ትምህርት ለመከለስ የግብአት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብርን አስመልክቶ ቅዳሜ ኅዳር ፪ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም በማኅበሩ ሥራ አመራር መሰብሰቢያ አዳራሽ ከባለ ድርሻ አካላት ውይይት ተካሄደ፡፡

በዚህ ውይይት ላይ ከፍተኛ የሥርዓተ ትምህርት ዝግጅት ባለሙያዎችና ከዘርፉ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ጥሪ የተደረገላቸው ምሁራን የተገኙ ሲሆን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ኃላፊ አቶ አበበ በዳዳ የነባሩን ሥርዓተ ትምህርት መከለስ ያስፈለገበትን መሠረታዊ ምክንያት በመተንተን ጉባኤውን አስጀምረዋል፡፡

አቶ አበበ የነባሩን ሥርዓተ ትምህርት ጉድለቶች በመተንተን የክለሳውን አስፈላጊነት ሲገልጹ፡- ነባሩ ሥርዓተ ትምህርት ዲጂታል ቴክኖሎጂን አለማካተቱ፣ ከተመደበው ጊዜና ቅደም ተከተል ጋር የተያያዙ ጉድለቶች መኖራቸው፣ ከማኅበረ ቅዱሳን ተቋማዊ ለውጥ አስተሳሰቦች አንጻር፣ የኢትዮጵያ ሥርዓተ ትምህርትና ሥልጠና የፖሊሲ ለውጥ ማድረጉና ትግበራ መጀመሩ፣ የሰ/ት/ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት ለውጥ ትግበራ መጀመር፣ ከሌሎችም ምክንያቶች አንጻር ተመዝኖ ነባሩን ሥርዓተ ትምህርት መከለስ አስፈላጊነቱ ታምኖበት ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት መስጠት ያስችል ዘንድ መዘጋጀት እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

በክፍል ሁለት ዝግጅት ሥርዓተ ትምህርቱን በመከለስ ረገድ ኃላፊነት ከተሰጣቸው የዘርፉ ምሁራን መካከል ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል “ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ላይ ተግባራዊ የሚደረገው የሥርዓተ ትምህርት ፍልስፍና” በሚል ዐቢይ ርእስ በአራት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርገው ያቀረቡ ሲሆን፡፡ እነዚህም፡- የሥርዓተ ትምህርት ትኩረት፣ የመምህሩ ሚና፣ የትምህርት አሰጣጥ መንገዶችና የማስተማሪያ ዘዴዎች፣ እንዲሁም የምዘናና የግምገማ ሥርዓት እንዴት መሆን እንዳለበት አብራርተዋል፡፡

ዲ/ን አንዱአምላክ በክፍል ሦስት ገለጻቸውም በሥርዓተ ትምህርት ሊታሰቡ የሚገባቸው የግቢ ጉባኤያት ነባራዊ ሁኔታዎች /Theoritical Approach/ ላይ ትኩረት አድርገዋል፡፡ በዚህም ማብራሪያቸው የሀገራችንን አዲሱን ሥርዓተ ትምህርት ታሳቢ ስለማድረግ፣ የተማሪዎች በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚቆዩበት ጊዜ መለወጥ፣ በቴክኒክና ሙያ ትምህርት አሰጣጥ ላይ የተለየ አቀራረብ መኖሩ፣ የመደበኛ ትምህርት ነባራዊ ሁኔታዎች፣ የተማሪዎች አስተዳደርና ሃይማኖታዊ ግንዛቤ፣ የሀገሪቱ  ውጥረትና ፖለቲካዊ የሥልጠና ፖሊሲዎች አለመረጋጋት፣ … እንዲሁም ሌሎች ነጥቦችን አንሥተው ሰፊ ገለጻ አድርገዋል፡፡

የክፍል አራት ገለጻው ደግሞን ከፍተኛ የትምህርት ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ቴዎድሮስ ሀብቴ “የአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት ጭብጦች /Thematic Areas/” በሚል ርእስ ላይ ያቀረቡ ሲሆን ከሥርዓተ ትምህርቱ ይዘት፣ ከመምህራን ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን፣ የሥርዓተ ትምህርቱ አቀራረብ፣ ምዘናና ሠርቲፊኬሽን ሂደት፣ የተማሪዎች ዳራ፣ ተቋማዊ ለውጥ እንዲሁም የነባሩ ሥርዓተ ትምህርት ግምገማና ሊሻሻሉ በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድረገው ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

ዶ/ር ቴዎድሮስ አክለውም በክፍል አምስት ላይ “የሥርዓተ ትምህርቱ የመማር ብቃቶች” በሚል ርእስ ባቀረቡት ማብራሪያ፡- ዶግማዊ የመማር ብቃት፣ ፖለቲካዊ የመማር ብቃት፣ ኢኮኖሚያዊ የመማር ብቃት፣ ማኅበራዊ የመማር ብቃትን ሌሎችንም ጉዳዮች አንሥተዋል፡፡

ቀጥሎም በሁለቱ የትምህርት ባለሙያዎች የቀረቡትን ዝርዝር ነጥቦች መነሻ በማድረግ በአራት መሠረታዊ የመወያያ ርእሰ ጉዳዮች ማለትም፡- ለተማሪዎች ምን ምን ይዘት ያላቸውን ትምህርቶች እናስተምራቸው? የትምህርት አቀራረቡ በምን መልኩ ይሁን? የማኅበረ ቅዱሳን የመምህራን ትምህርት ሥልጠና በተሻለ ሁኔታ እንዴት ይቅረብ? የምዘናና የምስክር ወረቀት አሰጣጥ አስመልክቶ ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡

በመጨረሻም ከታዳሚው የቀረቡትን አስተያየቶች በመቀበል ጠቃሚ ግብአቶችን እንዳገኙና በአዲሱ ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ሊካተቱ የሚገባቸው ነጥቦችን በመለየት እንደሚሠሩ የሥርዓተ ትምህርት ዝግጅት ባለሙያዎቹ በመግለጽ ውይይቱ ተጠናቋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለመጀመሪያ ጊዜ ለግቢ ጉባኤት ተማሪዎች የሚሆን ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ተግባራዊ ያደረገው በ፲፱፻፺፮ ዓ.ም ሲሆን ከስድስት ዓመታት ቆይታ በኋላ በተደረገ የዳሰሳ ጥናት ሥርዓተ ትምህርቱን የበለጠ ውጤታማና ዘመኑን የዋጀ አድርጎ ለማቅረብ አሁን እየተሠራበት ያለውን ሥርዓተ ትምህርት በ፳፻፪ ዓ.ም ተግባራዊ ማድረጉ ይታወሳል፡፡

ለግቢ ጉባኤያት ተተኪ መምህራን እና አመራሮች ሥልጠና ተሰጠ

በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ከማእከላትና ግቢ ጉባኤያት ጋር በመተባበር ከሐምሌ ፩ – ፴ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ድረስ  ለተተኪ መምህራን የደረጃ ሁለት  እና ለአመራሮች የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና መሰጠቱን በማኅበረ ቅዱሳን ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና የአቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል አስታወቀ፡፡

ሥልጠናው በሀገር ውስጥ በሚገኙ ስድስት ማስተባበሪያዎች በ፲ ሥልጠና ማእከላት የተሰጠ ሲሆን ፫፻፸፩ የደረጃ ሁለት ተተኪ መምህራንና ፫፻፴፬ አመራሮች መሳተፋቸው የተጠቀሰ ሲሆን   በደረጃ ሁለት የመምህራን ሥልጠና ከወሰዱት መካከል ፷፩ መምህራን በአፋን ኦሮሞ የሠለጠኑ መሆናቸውን ዋና ክፍሉ ገልጿል፡፡

ተተኪ መምህራኑ ዐሥራ አንድ የትምህርት ዓይነቶችን ማለትም ትምህርተ ሃይማኖት፣ ነገረ ማርያም፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እና ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ ነገረ ቅዱሳን፣ ክርስቲያናዊ ሕይወት እና ሥነ ምግባር፣ ሐዋርያዊ ተልእኮ እና የስብከት ዘዴ፣ ትምህርተ አበው፣ ኦርቶዶክሳዊ የጾታ ትምህርት እና የማማከር አገልግሎት፣ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያን ነባራዊ ሁኔታዎች እና የሰባክያነ ወንጌል ድርሻ በሚሉ ትምህርቶች ለአንድ ወር ሲሠለጥኑ ቆይተው ተመርቀዋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት አመራሮች ሥልጠናም ለአንድ ሳምንት የተሰጠ ሲሆን የመሪነት ክህሎት፣ ቤተ ክርስቲያን ማን ናት? ኦርቶዶክሳዊ ሕይወትና ክህሎቱ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአመራርነት ሚና ትናንት፣ ዛሬ እና ነገ፣ ግቢ ጉባኤያትና መገለጫ ጠባዮቻቸው፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ፣ ማኅበረ ቅዱሳን እና አገልግሎቱ በሚሉ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ ሥልጠናው እንደተሰጣቸው በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ማደራጃና የአቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል ለዝግጅት ክፍላችን ገልጿል፡፡

ለተተኪ መምህራኑና ለአመራሮቹ ከተሰጡት ሥልጠናዎች በተጨማሪ ሠልጣኞቹ ለሚያነሷቸው ጥያቆዎች ምላሽ፣ የምክክር እና የውይይት መርሐ ግብሮች ተካሂደዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ውስጥ በሚገኙ ፬፻፴፩ እና በውጭ ሀገራት በ፳፫ ግቢ ጉባኤያት፣ በአጠቃላይ በ፬፻፶፬ ግቢ ጉባኤያት መንፈሳዊ ትምህርት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በክረምት ምን ይጠበቅባቸዋል?

አሸናፊ ሰውነት

ግቢ ጉባኤያት ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች በዓለማዊና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ሆነው ሀገርንና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በታማኝነት ያገለግሉ ዘንድ ራሳቸውን የሚያዘጋጁበትና ክርስትናን በተግባር የሚገልጹበት ቦታ ነው።

ወጣትነት የምንለው ደግሞ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ መሠረት ከሃያ እስከ ዐርባ ዓመት ያለው ዕድሜ ነው፡፡ይህ የዕድሜ ክልል የእሳትነት ባሕርይ ጎልቶ የሚታይበት ጊዜ ሲሆን በአግባቡ ከተጠቀምንበት ከራስ አልፎ ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በማከናውን መልካም ፍሬን ማፍራት የሚቻልበት ወርቃማ ጊዜ ነው። ነገር ግን በተቃራኒው የወጣትነት ዕድሜን በመልካም መንገድ መምራት ካልተቻለ ከራስ አልፎ ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን መጉዳትን ያስከትላል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ግን የመንፈሳዊ ሕይወትን ጉዞ ጀምረዋልና ከራሳቸው አልፈው ለሌላው በመኖር እነርሱ የጀመሩትን መንፈሳዊ ሕይወት ጓደኞቻቸውም እንዲጀምሩና የክርስቶስ የፍቅሩን ጣዕም እንዲቀምሱ በማድረግ ኦርቶዶክሳዊና ማኅበራዊ ግዴታቸውን መወጣት ይገባቸዋል። እነዚህ የሩቅ መንገደኞች በክረምት ወቅት መደበኛ ትምህርታቸው ለዕረፍት በመዘጋቱ በዚህ ወቅት ምን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል? ስንል ከሚጠበቅባቸው ተግባራት ውስጥ ሁለቱን እንመለከታለን።

. መማር፡- እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ዐዋቂ አድርጎ ፈጥሮታል፡፡ ዕለት ዕለት በሚያደርገው እንቅስቃሴም አዳዲስ ነገሮችን የማወቅ፣ ክፉውንና ደጉን የመለየት ነፃነት ተሰጥቶታል፡፡ ነገር ግን ይህንን ስጦታ የሚጠቀሙበት ጥቂቶች ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት በጎውን በመተው ክፋትንም በማድረግ ኃጢአትን በራስ ላይ በማንገሥ እግዚአብሔርን የሚያሳዝኑ ብዙዎች ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “ሕዝቤ ዕውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቷል” እንዲል እስራኤላውያን ለተለያዩ የኃጢአት ሥራዎች ራሳቸውን አሳልፈው በመስጠታቸው እግዚአብሔር በነቢዩ ሆሴዕ ላይ አድሮ ገሥጿቸዋል፡፡ (ሆሴ.፬፥፮) አባቶቻችንም “ከመጠምጠም መማር ይቅደም” በማለት እንደሚናገሩት በዘመናችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከሚፈትናት ነገር አንዱ የምእመናን ስለ ሃይማኖታቸው ለመማር የሚያደርጉት ጥረት አነስተኛ መሆን ነው፡፡

ለመማር ጥረት የሚያደርግ ትውልድ ያውቃል፣ የሚያውቅ ደግሞ በቀላሉ ለክፉ ሥራ አይጋለጥም፤ ዘወትር ለመልካም ሥራ ይተጋል እንጂ፡፡ ስለዚህ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች በዚህ ዘመን በፍጥነት እየተለዋወጠች ባለች ዓለም ላይ እንደ አንድ ኦርቶዶክሳዊ የድርሻን ለመወጣት በሚደረግ እንቅስቃሴ ውስጥ በመሳተፍ ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች መንገዱን ማሳየትና ማሳወቅ  እንደ ግዴታ ሊቆጥሩት ይገባል። የማወቂያ አንዱ መንገድ ደግሞ መማር ሲሆን ዕውቀት ደግሞ ስለ አንድ ነገር ያለን መረዳት ወይም ግንዛቤ ነው፤ ዕውቀት ሥጋዊና መንፈሳዊ ተብሎ በሁለት ይከፈላል።

መንፈሳዊ ዕውቀትን ስንመለከት ለማገልገልም ሆነ ለመገልገል አስፈላጊ ነው። ከሐዋርያትም ታሪክ የምንማረው ይህንኑ ነው። በቅድሚያ ከጌታችን እግር ሥር ተማሩ፤ የተማሩትን ደግሞ   በቃልና በተግባር ፈጸሙት። የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችም በግቢ ቆይታቸው የተማሩትን መንፈሳዊ   ትምህርት ለማጠናከር በደረጃቸውና እንደ አካባቢያቸው ምቹ ሁኔታ በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በአብነት ትምህርት ቤቶች የሚሰጡ ትምህርቶችን ጊዜ ሰጥቶ መማር ይጠበቅባቸዋል። ይህ ከሆነ በመነሻችን ላይ እንደ ጠቀስነው በግቢ ጉባኤ ቆይታቸው በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ሆነው ለመውጣት የሚያደርጉትን ሩጫ ያቀልላቸዋል።

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ወጣቶች እንደመሆናቸው መጠን ከስሜታዊነት ርቀው ዕውቀትን ፍለጋ በሚያደርጉት ጥረት ውስጥ ከሐሰተኛ ትርክቶችና የምዕራባውያን አእምሮ በራዥ ትምህርቶች በመራቅ በኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ላይ ሊገነቡ ይገባል፡፡ የቀደምት ኦርቶዶክሳውያን አባቶቻችን ታሪክ የሚነግረን ዕውቀትና ጥበብን አጥብቆ ፈላጊዎች መሆናቸውን ስለሆነ እነርሱን አርአያ በማድረግ የወደፊት የሕይወት አቅጣጫቸውን በኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ላይ መገንባት ይጠበቅባቸዋል፡፡

ከላይ የተነሡት መሠረታዊ ጉዳዮችን ወደ ተግባር ለመቀየር በሚደረግ ጥረት ውስጥ ችግሮች አይኖሩም ማለት አይደለም፡፡ ለምሳሌ፡- ስሜታዊነት፣ የዓላማ አለመኖር፣ የሚያስፈልጋቸውን   አለማወቅ፣ ቁርጥ ውሳኔ አለመወሰን፣ ነገሮችን በሥጋዊ ዓይን ብቻ ማየት፣ የአብነት ትምህርትን ለቤተ መቅደስ አገልግሎት ብቻ ነው ብሎ ማሰብና ሌላ ጊዜ እደርስበታለሁ ብሎ መዘናጋት፣ …  ተጠቃሾች ናቸው። የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች በዚህ ክረምት እነዚህንና ሌሎችም ከመንፈሳዊ ጉዟቸው ሊያደናቅፉ ከሚችሉ ነገሮች በመራቅ ለዕውቀት ልዩ ትኩረት በመስጠት መንፈሳዊ ሕይወታቸውን ሊያንጹ ይገባል፡፡

. ማገልገል፡- አገልግሎት እግዚአብሔርን የመውደዳችን አንዱ መገለጫ ነው። ማገልገል ስንል የግድ ሰንበት ትምህርት ቤት ገብተን አልያም ዐውደ ምሕረት ላይ አትሮንስ ተዘርግቶ ብቻ ላይሆን ይችላል። ቅዱስ ጳውሎስ አገልግሎትን “ስለዚህ ለጋስ ስጦታ ማንም እንዳይነቅፈን እንጠነቀቃለን፤ በእግዚአብሔር ፊት ብቻ ያይደለ ነገር ግን በሰው ፊት መልካምን ነገር እናስባለንና” በማለት ገልጦታል፡፡ (፪ኛቆሮ. ፰፥፳-፳፩) ስለዚህ ጊዜና ቦታ መርጠን ሳይሆን የትም ቢሆን መቼም የምናደርጋቸውን ነገሮች ሁሉ በሥርዓትና በአግባቡ ማድረግ ተገቢ ነው።

ይህም ማለት መንፈሳዊ አገልጋይ በመንፈሳዊና በማኅበራዊ ሕይወቱ ራሱን በመጠበቅ ለሰዎች እንቅፋት ሊሆኑ ከሚችሉ ድርጊቶችም በመራቅ ሊኖር ይገባል፡፡ ምክንያቱም ክርስትና በቃልም፣ በተግባርም የሚገልጥ ነውና፡፡ አገልጋይ ልቡናው በፍቅረ እግዚአብሔር የተሞላ ከእግዚአብሔር ጋር መኖር መልካም እንደሆነ ቀምሶ ያየና ሌሎችንም ወደዚህ ሕይወት እንዲመጡ የሚጋብዝ ነው። ይህንን ለማድረግ ደግሞ ቀጠሮ አያስፈልግም፤ ምክንያቱም የመዳን ቀን አሁን ነውና።

በአገልግሎት ውስጥ ያለ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት እንደ እግዚአብሔር ቃል እንዳይመላለስና አገልግሎቱንም በትጋት እንዳይፈጽም ከራሱ፣ ከሰይጣንና ከአካባቢ በሚመነጭ ፈተና ሊፈተን ይችላል፡፡ አንድ ክርስቲያን እነዚህ ሁሉ የግድ ሊጠብቃቸው የሚገቡ ናቸው እንጂ አገልግሎት አልጋ በአልጋ ሊሆን እንደማይችል መረዳት ያስፈልጋል። ያ ቢሆን ኖሮ ቅዱሳን ሐዋርያት በመቀጠልም ሰማዕታት ብሎም ሐዋርያነ አበው ያ ሁሉ መከራና ሥቃይ ባለደረሰባቸውም ነበር።

ስለዚህ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ለአገልግሎት ያላቸውን አመለካከት በማስተካከልና ነገ አገለግላለሁ ከማለት ወጥተው በቅንነት ሊያገለግሉ ይገባል። ስለሚበሉት፣ ስለሚጠጡት፣ ስለሚለብሱት፣ ነገ ስለሚኖራቸው መኖሪያ ቤት፣ ስለሚይዙት መኪና፣ ስለ ሥልጣንና መሰል ነገሮች በማሰብ ቁሳዊ ብቻ መሆን ሳይሆን ለራሳቸውና ለሌሎች ድኅነት ሊተጉ ይገባል።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “አገልግሎት ስላለን አንታክትም” በማለት እንዳስተማረው (፪ኛቆሮ.፬፥፩) እንደ አባቶቻችን ዕለት ዕለት መጨነቅ የሚገባው ስለ የአብያተ ክርስቲያናት ጉዳይ መሆን አለበት። ለአንድም ሰው ቢሆን የድኅነትን መንገድ ማሳየትና መምራት ዋጋ ስላለው መድከም፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ላይም መሠማራት፤ የእግዚአብሔርን ቃል መናገር ብቻ ሳይሆን በተግባር ማሳየት ያስፈልጋል፡፡ አካሄዳችሁንም አይተው የማን ፍሬ እንደሆናችሁ ያውቃሉና እንደተባለው።

በመጨረሻ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች በክረምት ወቅት ማድረግ ስላለባቸው ጉዳዮች በተመለከተ መማርና ማገልገልን የሚሉትን ነጥቦች አነሣን እንጂ በርካታ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ይጠብቋቸዋል፡፡ እነዚህንም በማከናወን ሂደት ውስጥ ዓላማና ግብ ያላቸውን ዕቅዶች በማውጣት ለተግባራዊነቱም ቁርጥ ውሳኔና ጥረት በማድረግ፣ እግዚአብሔርን በጸሎት በመጠየቅና አገልግሎቱም ፍሬ ያፈራ ዘንድ በመትጋት ክረምቱን በመንፈሳዊ አገልግሎት ማሳለፍ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጾመ ፍልሰታ

በሳሙኤል ደመቀ

ጠቢቡ ሰሎሞን አስቀድሞ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤና ዕርገት በትንቢት ተናግሯል፡- “ወዳጄ ሆይ፥ ተነሺ ውበቴ ሆይ፥ ነዪ” በማለት (መኃ. ፪÷፲)፡፡ ፍልሰት ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መሔድ መወሰድ፣ መሰደድ፣ መፍለስ የሚል ፍቺ ይኖረዋል፡፡ ፍልሰታ ቃሉ የእመቤታችን ሥጋ ከጌቴ ሴማኒ ዕፀ ሕይወት ወደአለበት ወደ ገነት፤ ኋላም ከዕፀ   ሕይወት ሥር መነሣቱን የሚያመለክት ነው፡፡

የፍልሰታ ለማርያም ጾም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ካሏት ከሰባቱ የዐዋጅ አጽዋማት መካከል አንዱ ነው፡፡ ከነሐሴ ፩ እስከ ፲፭ ድረስ የምንጾመው ጾም ሲሆን ጀማሪዎቹም ቅዱሳን ሐዋርያት ናቸው፡፡ የጌታችን እናት የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ትንሣኤና ዕርገት ያዩ ዘንድ ጾመውታልና፡፡ የእመቤታችን ፍቅር እንዲበዛልን ልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከበረከቷ እንዲከፍለን፣ በዓለም ካለ መከራና ችግር በአማላጅነቷ ጥላ ከልሎ እንዲያሳልፈን ስለምንማጸንበት መምጣቱን በፍቅር የምንጠባበቀው የጾም ጊዜ ነው የፍልሰታ ለማርያም ጾም፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የአፅብ ለኵሉ፤ ሞትስ ለሚሞት ይገባዋል፤ የማርያም ሞት ግን ከሁሉ ያስደንቃል” በማለት እንዳመሰገነው እመቤታችን ከፍጥረት ሁሉ የምትከብር ከሁሉ ከፍ ያለች ብትሆንም በተፈጥሮ ከሰው ወገን ናትና እንደ ሰው ትሞትን ትቀምስ ዘንድ ስለሚገባ ቅዱሳን እያመሰገኗት በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩ ቀን ዐርፋለች።

ቅዱሳን ሐዋርያትም አስቀድሞ ሞቷ በመንፈስ ቅዱስ ስለተገለጸላቸው ከያሉበት ተሰባስበው  የተቀደሰ ሥጋዋን ገንዘው ለመቅበር ወደ ጌቴሴማኒ ሲሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇ ሞተ፣ ሞትንም ድል አድርጎ ተነሣ ይላሉ፤ አሁን ደግሞ እናቱ ሞታ ተነሣች እያሉ እንዳያስቸግሩን   አስከሬኗን በእሳት እናቃጥለው” በማለት በክፋት ተነሡ፡፡ ምክንያቱም የጌታችን ከሞት መነሣትና ማረግ በዓለም ሁሉ እየታመነበት ስለመጣ እርሷም እንደ ልጇ ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ያስተምራሉ በሚል ፍርሃት ነበር፡፡ ከአይሁድ ወገን የሆነ ታውፋንያ የተባለ ብርቱ ሰው የእመቤታችን የተቀደሰ ሥጋዋ ያረፈበትን ቃሬዛ ከቅዱሳን ሐዋርያት ለመንጠቅ ሲሞክር መልአከ እግዚአብሔር ተገልጾ በእሳት ሰይፍ እጆቹን ቆረጣቸው። ቅዱስ ጴጥሮስም ወደ  እመቤታችን ቢለምን በእመቤታችን አማላጅነት የታውፋንያ እጆቹ እንደነበሩ ተመልሰውለታል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ እመቤታችን በመላእክት ዝማሬ ታጅባ በደመና ነጥቆ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡  ይህንንም ከወንጌላዊው ከቅዱስ ዮሐንስ በቀር ለሌሎች ቅዱሳን ሐዋርያት ለጊዜው አልተገለጠላቸውም ነበር። ቅዱሳን ሐዋርያትም ለእመቤታችን ካላቸው ፍቅር የተነሣ ለምን አልቀበርናትም? ለምንስ የሥጋዋ ምሥጢር ለቅዱስ ዮሐንስ ተገልጾ ለእኛ ይሰወረናል? በማለት መንፈሳዊ ቅናት እየቀኑና እያዘኑ ቆይተው ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምሮ በጾምና በጸሎት ቆይተው ነሐሴ ፲፬ ቀን ሥጋዋ ተሰጥቷቸው በታላቅ ክብርና ምስጋና በጌቴሴማኒ ቀበሯት። በ፫ኛውም ቀን ነሐሴ ፲፮ በልጇ ሥልጣን ከተቀበረችበት ተነሥታ በታላቅ ክብር ዐርጋለች።

ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አርጋኖን በተባለ ድርሰቱ እመቤታችንን በከበሩ ደንጊያዎች እየመሰለ የሚያመሰግንበት ክፍል አለው፡፡ በዚህ ምስጋናው በምሳሌ እመቤታችንን ካመሰገነበት የደንጊያ ዓይነቶች አንደኛው የደወል ደንጊያ ነው፡፡ ለምን የደወል ደንጊያ እንዳላት ሲያብራራ እንዲህ ይላል፡- “አንዲት በምጥ የተያዘች ሴት የደወል ደንጊያ ሲመታ ብትሰማ ልቡናዋ በድምጹ ውበት ስለሚመሰጥ ምጧን እንደምትረሳና እስከምትወልድ ድረስ ሕመሙ አይሰማትም” በማለት ጠቅሶ ሰማዕታትም ከእመቤታችን ፍቅር በመነጨ የሚደርስባቸውን መከራና ሕማም እንደሚዘነጉት ይገልጻል፡፡ በፍልሰታም እንደዚሁ ነው፡፡ ከሕፃናት እስከ አረጋውያን ያሉ ወንዶችም ሴቶችም ለእመቤታችን ካላቸው ፍቅር በመነጨ ረኀቡና ጥሙ ሳይታወቃቸው ሳይመረሩ በደስታ ይጾሙታል፡፡

የጾሙ ጣዕም የመብልን አምሮት የሚያስንቅ ነው፡፡ መንፈሳዊነት በሰውነታችን እንዲሰለጥን ያደርጋል፡፡ ይኸውም የእመቤታችን በረከት ውጤት ነው፡፡ ጾሞ ለመጠቀም ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር

ክፍል ሦስት

በእንዳለ ደምስስ

“ትምህርቴን በስኬት እንዳጠናቅቅ የረዳኝ ግቢ ጉባኤ ነው” (ዲ/ን አሰፋ አያሌው)

የክፍል ሦስት እንግዳችን ምሥራቀ ግዮን ኮሌጅ (የግል ኮሌጅ) በነርሲንግ ትምህርት ክፍል ተመራቂ የሆነው ዲ/ን አሰፋ አያሌው ነው፡፡ ዲ/ን አሰፋ ደሴ ከተማ ውስጥ ከሚገኘው ምሥራቀ ግዮን ኮሌጅ (የግል ኮሌጅ) በነርሲንግ ትምህርት ክፍል ከኮሌጁ ሦስት ነጥብ ዘጠኝ ሰባት (3.97) በማምጣትና ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ለመሆን በቅቷል፡፡

ዲ/ን አሰፋ የምሥራቀ ግዮን ጉባኤ ተሳታፊ የነበረ ሲሆን ከትምህርቱ በተጨማሪ የአብነት ትምህርቱን ተከታትሎ ዲቁና ተቀብሏል፤ ዐራተኛ ዓመት ላይ ደግሞ የተመራቂዎች ኮሚቴ (Graduation Committee) ሰብሳቢ ሆኖም አገልግሏል፡፡

ኮሌጅ ከገባ በኋላ የገጠመውን ሲገልጽ፡- “ኮሌጅ እንደገባሁ ግቢ ጉባኤ ውስጥ ለመሳተፍ አልሞከርኩም፡፡ ነገር ግን ከሁለተኛ ዓመት ጀምሮ ያለማቋረጥ ነው በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠውን ተከታታይ ትምህርት ለመማር የቻልኩት፡፡ ጊዜዬን በእቅድ እንድጠቀምና ከመደበኛ ትምህርቴ ጋር አጣጥሜ እንድጓዝ፣ በስኬታማነት እንዳጠናቅቅም የረዳኝ ግቢ ጉባኤ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ግቢ ጉባኤ ውስጥ መሳተፍ እንደጀመርኩ የአብነት ትምህርቱንም ጎን ለጎን መከታተል ጀመርኩ፡፡ በዚህም መሠረት የእግዚአብሔር ፈቃድ ሆኖ ተሳክቶልኝ ዲቁና ለመቀበል በቅቻለሁ፡፡ አሁንም ከግቢ ከወጣሁ በኋላ የአብነት ትምህርትን ለመማር እንደ እቅድ ይዣለሁ፡፡ “ በማለት ግቢ ጉባኤ በሕይወቱ ውስጥ ያሳረፈውን በጎ ተጽእኖ ይገልጻል፡፡

የጊዜ አጠቃቀምን በተመለከተም፡- “የመጀመሪያ ዓመት ላይ ጊዜዬን በአግባቡ ለመጠቀም አልሞከርኩም በተቃራኒው ሌሎች ጓደኞቼን ለመምሰልና በዙሪያዬም የነበሩ ሊያዘናጉ ከሚችሉ ነገሮች ለመራቅ እንኳን ሙከራ አላደርግም ነበር፡፡ ነገር ግን ግቢ ጉባኤ መሳተፍ ከጀመርኩ በኋላ በጊዜ አጠቃቀም ዙሪያ ምክርና ትምህርትም ይሰጠን ስለነበር በትክክል ተጠቅሜበታለሁ፡፡ ዐራተኛ ዓመት ላይ ግን የተመራቂ ተማሪዎች ኮሚቴ ሰብሳቢ (Graduation Committee) ሆኜ ማስተባበር ተጨምሮብኝ ስለነበር ትንሽ ሁሉንም አጣጥሞ ለመጓዝ ከብዶኝ ነበር፡፡ መደበኛ ትምህርቴ፣ ግቢ ጉባኤ፣ የአብነት ትምህርቴ፣ ጥናት እና የተመራቂ ተማሪዎች ኮሚቴ ሰብሳቢ መሆኑ አጨናንቆኝ የነበረ ቢሆንም እግዚአብሔር ረድቶኝ ከዩኒቨርሲቲው ሦስት ነጥብ ዘጠኝ ሰባት አጠቃላይ ውጤት በማምጣት የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ለመሆን በቅቻለሁ፡፡ ግቢ ጉባኤ በመንፈሳዊ ሕይወቴ ጠንክሬ መጓዝ እንድችልና ውቴታማ ሆኜ ከግቢው እንደወጣ አስችሎኛል”ሲል ተሞክሮውን ገልጾልናል፡፡

ዲ/ን አሰፋ ያጋጠሙትን ችግሮች በተመለከተ ሲገልጽም “ዐራተኛ ዓመት ላይ የመመረቂያ ዓመት ስለነበር የጊዜ እጥረት እየገጠመኝ እየተጨናነቅሁ በአግባቡ መጓዝ አቅቶኝ ነበር፡፡ በተለይም ከምረቃ ጋር ተያይዞ በርካታ ሥራዎችን እንሠራ ስለነበር በከፍተኛ ሁኔታ የጥናት ጊዜዬን ይሻማብኝ ነበር፡፡ በተጨማሪም ከዩኒቨርሲቲው መውጫ ፈተና (Exit Exam) ዝግጅት ጋር ተያይዞ ማጥናትን ይጠይቅ ስለነበር ከባድ ጊዜ ለማሳለፍ ተገድጄ ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር አግዞኛልና ጎዶሎነቴን እየሞላ በጥሩ ውጤት ለማጠናቀቅ ችያለሁ፡፡”

ዲ/ን አሰፋ እርሱ ያለፈበትን ሕይወት መነሻ በማድረግ ባስተላለፈው መልእክትም “ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚገቡ ተማሪዎች የምመክረው ከመጀመሪያው ጀምሮ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ለመሳተፍ ወስነው መምጣትና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ነው፡፡ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ማሳለፋቸው ጠንካሮችና የዓላማ ሰው እንዲሆኑ ያስችላቸዋል፡፡ እኔ በመጀመሪያ ዓመት ላይ በግቢ ጉባኤ አለመሳተፌ ውጤቴ ላይ ዋጋ አስከፍሎኛል፡፡” ሲል መልእክቱን አስተላልፏል፡፡

ልዩ ማስታወሻ ከአዘጋጁ፡-

ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ አንስቶ ላለፉት ሠላሳ አንድ ዓመታት ግቢ ጉባኤ ላይ በመሥራት የተጣለበትን አደራና ኃላፊነት ለመወጣት ክፍተኛ ጥረት አድርጓል፣ በማድረግም ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም ጥረቱ በርካቶችን በየከተኛ ትምህርት ተቋማት መሠረታዊ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በማስተማር በአባቶች ቡራኬና በአደራ መስቀል እያስመረቀ ይገኛል፡፡ ብዙዎችም ለውጤታማነታቸው ማኅበሩ በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠውን መንፈሳዊ ትምህርት በመከታተላቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲያውቁ፣ እምነታቸውን ጠንክረው እንዲይዙ፣ በሥነ ምግባር ታንጸው በየተሠማሩበት ቦታና ሙያ ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን በማገልግል የድርሻቸውን መወጣት እንዲችሉ እንደረዳቸው ይመሠክራሉ፡፡

የተከበራችሁ የድረ ገጻችን ታዳሚዎች በተከታታይ በሦስት ክፍል የወንድሞችና የእኅቶች ይግቢ ጉባኤ ተሞክሮ ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ነውና ወደፊት የሚገቡ ተማሪዎች አርአያነታቸውን ተከትለው እንዲጓዙ ያደርጋቸዋል በሚል ከብዙ በጥቂቱ ያቀረብንበትን ዝግጅት በዚሁ እንቋጫለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!

በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት እንዲሁም ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ፡- እግዚአብሔር አምላካችን በይቅርታውና በምሕረቱ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዐሥራ አምስት ዓመተ ምሕረት የድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ።

ወእምኵሉሰ ዘይቀድም ተፋቀሩ በበይናቲክሙ በምልአ ልብክሙ እስመ ተፋቅሮ ይደፍኖን ወይደመስሶን ለኵሎን ኃጣውእ፤ ከሁሉ አስቀድሞ በሙሉ ልባችሁ እርስ በርሳችሁ ተፋቀሩ፣ መፋቀር ሁሉንም ዓይነተ ኃጢአት ይሸፍናልና ይደመስሳልምና” (፩ጴጥ. )

ሁላችንም እንደምናውቀው የቅዱስ ወንጌል አስተምህሮ መሠረትና ጣርያ ወለልና ግድግዳ በፍቅርና በፍቅር ብቻ የተገነባ ነው፤ ፍቅር እግዚአብሔር ዓለምን ያዳነበት መድኃኒት ነው፣ ፍቅር የጥላቻና የመለያየት ግንብን ንዶ ይቅርታንና አንድነትን የሚገነባ ጠንካራ ዓለት ነው፤ ፍቅር መጽናናትንና ደስታን የሚያፈራ ጣፋጭ ተክል ነው፤ በፍቅር ለፍቅር የሚደረግ ሁሉ ፍሥሐን እንጂ ጸጸትን አያስከትልም፤ በመሆኑም በሰብኣዊ ድክመት ምክንያት ሰዎች ፍቅርን ሙሉ በሙሉ በሚፈለገው ደረጃ ባንጠብቀውም በዓለማዊም ሆነ በመፈንሳዊ ሕይወት ከፍቅር የበለጠ ጠቃሚ ነገር የለም፤ ፍቅር የማይሻርና ለዘላለሙ ጸንቶ የሚኖር እንደሆነ በቅዱስ መጽሐፍ ተመዝግቦአል፤ ምክንያቱም ፍቅር ከሞት ቡኋላም ቢሆን በእግዚአብሔር መንግሥት ይቀጥላልና ነው፤ ዛሬ የሚጀመረው የድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታም በፍቅር ለፍቅር የተፈጸመ ነው፣ ይኸውም ቅዱሳን ሐዋርያት የድንግል ማርያምን የማረፊያ ቦታ ለማየት ሲሉ የጾሙት ጾም ነው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት የገለፁት ፍቅረ ድንግል ማርያምን ብቻ ሳይሆን ያረፈችበትንም ቦታ ጭምር ያመለከተ ነበረ፥ ይህ ሊሆን የቻለው ከልብ የሆነ እውነተኛ ፍቅር በሐዋርያት ዘንድ ስለነበረ ነው፡፡

እኛም ዛሬ የምንጾመው ይህንን የማርያም ጾም እንደ አበው ሐዋርያት ፍቅረ ድንግል ማርያም በልባችን ውስጥ ተተክሎ ስላለ ነው፤ እግዚአብሔር በፍቅርና በሃይማኖት የሚቀርብለትን ሁሉ ይቀበላልና የሐዋርያትን ጾምና ጸሎት ተቀብሎ ጥያቄአቸውን መልሶአል፡፡ ዛሬም ይህንን ጾም የምንጾመው እግዚአብሔር ጾማችንን ተቀብሎ የልባችንን መሻት ይፈጽምልናል ብለን ነው፣ በፍቅርና በሃይማኖት እስከ ጾምን ደግሞ እግዚአብሔር ይቀበለናል። 

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!

እንደ እግዚአብሔር ቃልም እንደ አባቶቻችን ትውፊትም የጾመ ፍልሰታ ጾም ሲጾም የበደለ ይቅርታ ጠይቆ፤ ተገቢውንም ካሣ ከፍሎ፣ ቂም በቀሉን አሰርዞ፣ ፍቅርን መሥርቶ ነበረ፤ የተበደለም በበኩሉ ዕርቅን አውርዶ፣ ይቅርታን ሰጥቶ የአእምሮ ማለስለሻና ማስረሻ የሆነውን ካሣውን ተቀብሎ ቂሙንና በቀሉን ከአእምሮው አውጥቶና አጽድቶ፣ ለእግዚአብሔር ስል ከልቤ ይቅር ብያለሁ ብሎ፤ ስመ እግዚአብሔርን ጠርቶ በፍቅር ይታረቃል፡፡

በዚህ ሁኔታ ፍጹምና ልባዊ ፍቅር ተይዞ ሲጾም ሁሉም ዓይነት ኃጢአት ሙሉ በሙሉ ይደመሰስለታል። እግዚአብሔርም ይቅርታ ጠያቂውንም፣ ይቅርታ ሰጪውንም አሸማጋዩንም ይባርካል ።ማኅበረ ሰቡም በዚህ ቅዱስና ሃይማኖታዊ ባህልና ትውፊት ተጠብቆ ለብዙ ዘመናት አንድነቱንና ሃይማኖቱን ወንድማማችነቱንና ነጻነቱን አስጠብቆ እስከ ዛሬ ደርሶአል፤ ይህ ለሀገራችን ታላቅ የሆነ የእግዚአብሔር በረከት ነበረ፤ ይህ እውነተኛ በረከት በአሁኑ ጊዜ ቸል በመባሉ ፈተናችን በዝቶአል፤ እንደ እውነቱ ከሆነ ሰው በኃጢአት ከወደቀበት ጊዜ ጀምሮ ጥልና መገዳደል በየትኛውም ጊዜ፣ በየትኛውም ሀገር በየትኛውም ማኅበረ ሰብ ይከሠታል፣ ዛሬም በሀገራችን በተፈጠረው አለመግባባት ከባድ ችግር ተፈጥሮአል፣ የሚያስገርመው ነገር ቢኖር እንዴት እንደ ባህላችንና እምነታችን በቀላሉ በዕርቅና በይቅርታ ማስተካከል አቃተን የሚለው ነው፤ የዘመናችን ልዩ ነገር ይህ ነው፤ ለዚህም ብዙ የተለያየ ምክንያት ሊኖረው ይችላል፤ በሃይማኖት ዓይን ሲታይ ግን ለእግዚአብሔር ቃል የምንሰጠው ክብር በእጅጉ ስለተቀነሰ ነው የሚል ሆኖ ይገኛል፤ ይህ ዝንባሌ አሁን ላለውም ሆነ ለሚመጣው ትውልድ አደገኛ ስለሆነ የኦርቶዶክስ ሕዝበ ክርስቲያንም ሆነ ሌሎቹ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ይህንን በጥልቀት ሊያጤኑትና ሊያርሙት ይገባል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናንት!

ሽማግሌ የሀገር በረከት ነው፤ አስታራቂ ሽማግሌ የችግር ሐኪምና ፈዋሽ ነው፤ የፍቅርና የተግባቦት መሐንዲስም ነው፤ በእግዚአብሔርም “የሚያስታርቁ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው” ተብሎ ውዳሴ ተችሮአቸዋል፣ እነዚህን ሽማግሌዎች ተጠቅመን ችግሮቻችንን መፍታት ጊዜው የሚጠይቀው አስገዳጅ ጉዳይ ሆኖአል፤ ሁሉም ታየ፤ ሁሉም ተሞከረ፤ ዘላቂ መፍትሔ ሲያመጣ ግን አልታየም፤ እንዲያውም ችግሩ ወደ ሃይማኖት ተዛምቶ ቤተ ክርስቲያንም የገፈቱ ቀማሽ ለመሆን ተገዳለች፡፡

በተጨባጭ እንደሚታወቀው ሕዝብንና ሃይማኖትን ነጣጥሎ ሰላምን ማረጋጋጥ ከቶውኑ ሊታሰብ አይችልም፤ ምክንያቱም ሕዝብ የሃይማኖቱ ቤተሰብ ነው፣ ሃይማኖቱም በሕዝቡ መንፈስ ውስጥ ነግሦ የሚኖር መለኮታዊ ኃይል ነውና፣ ከዚህ አንጻር “ወልድ ሲነካ አብ ይነካ እንደሚባለው ሕዝቡ ሲነካ ሃይማኖቱ ይነካል፤ ሃይማኖቱ ሲነካ ደግሞ ሕዝቡ ይነካል፤ በመሆኑም በተካሄደው ግጭት ብዙ ነገሮች መመሳቀላቸው የማይካድ ቢሆንም ችግሩ በዕርቅና በካሣ በይቅርታና በመተው ካልተዘጋ ለማንም ስለማይበጅ ከባድ ጉዳት የደረሰባቸው ወገኖች ለዕርቅ ዝግጁ እንዲሆኑ፣ የበደሉም እንዲክሱ የሀገር ሽማግሌዎችም የማስታረቅ ሥራን በሐቅ በገለልተኝነትና ዕንባን በሚያደርቅ ስልት እንዲሸመግሉ መንግሥትም የበኩሉን ድጋፍ እንዲያደርግ በዚህ አጋጣሚ በእግዚአብሔር ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም

የገጠመንን ፈተና ሁሉ ሊያቀልልንና ሊያስወግድልን የሚችል እግዚአብሔር ስለሆነ በዚህ የጾመ ማርያም ወቅት ምእመናን በተመሥጦና በንሥሐ ሕይወት ለእግዚአብሔር በመንበርከክ ስለ ሰላምና ፍቅር እንዲማፀኑ፣ ካላቸውም በረከት ለተራቡትና ለተፈናቀሉት እንዲለግሱ ሁሉም ወገኖች በሆነው ነገር ይብቃን ብለው ወደ ሰላማዊ አማራጭ እንዲቀርቡ በእግዚአብሔር ስም አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

መልካም የጾመ ማርያም ሱባዔ ያድርግልን

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

 ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ነሐሴ 2015 ..

ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር

ክፍል ሁለት

በእንዳለ ደምስስ

“ግቢ ጉባኤ ባይኖርና ወደ ቤተ ክርስቲያን ባንመላለስ በዓለም ጠፍተን እንቀር ነበር”

(ዶ/ር ምንተስኖት መንግሥቱ)

የተከበራችሁ የማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ድረ ገጽ ተከታታዮች፡- “ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር” በሚል ርእስ በክፍል አንድ ዝግጅታችን ከቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤያት ከዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ ተመራቂዎች 3.99 ከፍተኛ ነጥብ በማምጣት የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ከሆነችው እኅታችን ውብነሽ ለማ ጋር ያደረግነውን አጭር ቆይታ አቅርበንላችኋል፡፡ በክፍል ሁለት ዝግጅታችን ደግሞ ከሌሎች ተመራቂዎች ጋር የምናደርገውን ቆይታ ትከታተሉ ዘንድ እነሆ፡-

ዶ/ር ምንተስኖት መንግሥቱ በ፳፻፲፭ ዓ.ም ከጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ትምህርት ክፍል በእንስሳት ሕክምና ትምህርቱን አጠናቋል፡፡ በሦስት ነጥብ ዘጠኝ ስምንት (3.98) አጠቃላይ ውጤት ዩኒቨርሲቲው ያዘጋጀውን ዋንጫና ሜዳሊያ ተሸላሚ ለመሆን በቅቷል፡፡ በዩኒቨርሲቲው እና ስለ ግቢ ጉባኤ ቆይታው ጠይቀነዋል፡-

ዶ/ር ምንተስኖት እንዲህ ይገልጸዋል፡- “በዩኒቨርስቲ ቆይታዬ የምችለውን ያህል ጥረት ማድረጌ እንዳለ ሆኖ የእግዚአብሔር እገዛና ቸርነት አልተለየኝም፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ሳለሁም በቅድመ ግቢ ጉባኤ እሳተፍ ስለነበር ዩኒቨርሲቲ ስገባ ቀጥታ ያመራሁት ወደ ግቢ ጉባኤ ነው፡፡ እንዲያውም እኔና ጓደኞቼ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ስንሄድ በአባቶች ቡራኬ ነበር የተሸኘነው፡፡ በተጨማሪም በቅድመ ግቢ ጉባኤ ውስጥ ከእኛ ቀድመው ዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ወንድሞችና እኅቶች ተጋብዘው ተሞክሯቸውን ያካፍሉን ነበር፡፡ ወንደሞችና እኅቶችም በጥሩ ሁኔታ ነው የተቀበሉኝ፡፡ በዙሪያዬም መልካም ኦርቶዶክሳውያን ቤተሰቦችና ዩኒቨርሲቲ ስገባም ያጋጠሙኝ ጓደኞቼ ለቤተ ክርስቲያንና ለትምህርታቸው ትኩረት የሚሰጡ ስለነበሩ ለውጤታማነቴ አስተዋጽኦ አድርገዋል ማለት እችላለሁ፡፡ በቆይታዬም ለትምህርቴና ለቤተ ክርስቲያን ቅድሚያ በመስጠቴ ለውጤት በቅቻለሁ” ሲል ይገልጻል፡፡

ጓደኛን በተመለከተም “በዩኒቨርሲቲ ቆይታችን ውስጥ ጓደኛ ትልቁን ድርሻ ይወስዳል፡፡ ተመሳሳይ ዓላማ ከሌላቸው ተማሪዎች ራስን ማራቅም ይገባል፡፡ ወደ ዩኒቨርሲቲ ስሄድ ዓላማዬ መማር ነው፡፡ መማር ብቻም ሳይሆን ወደፊት ለሚኖረኝ ሕይወት መሠረት የምጥልበት ስለሆነ ከሌሎች የተሻለ ሆኜ ለመገኘት መሥራት እንዳለብኝ ራሴን አሳምኜ ነው የገባሁት፡፡ ስለዚህ ከማይመቹ እና የሕይወት አቅጣጫዬን ከሚያስቱ ተማሪዎች መራቅ ነበረብኝ፤ ይህንንም አድርጌዋለሁ፡፡ ጓደኞቼ ጥሩዎች ስለነበሩ ጅግጅጋ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን እንሄዳለን፤ መርሐ ግብሮች አያመልጡንም፣ ቅዳሜና እሑድ ደግሞ በግቢ ጉባኤያችን የተዘጋጀውን ጉባኤ እና ተከታታይ ትምህርት እንሳተፋለን፤ ቀሪውን ጊዜ ደግሞ ለትምህርት እናውለዋለን፡፡ በቃ የእኔ ሕይወት በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ይህ ነበር ማለት እችላለሁ” በማለት ቆይታውን ይገልጻል፡፡

ከጊዜ ጋር የነበረውን አጠቃቀምም በተመለከተ “አንድም ደቂቃ ትሁን ዋጋ አላት” ይላል ዶ/ር ምንተስኖት፡፡ አያይዞም “የገባሁበት ትምህርት ክፍል ከፍተኛ ንባብ የሚጠይቅ ክፍል ነው፡፡ ስለዚህ አብዛኛውን ጊዜዬን የማሳልፈው በማንበብ ነው፡፡ ይህንንም በእቅድ መምራት ያስፈልጋል፡፡ አንድ ጊዜ ካቀድከው እቅድ ከተደናቀፍህ ወደ ትክክለኛው አቅጣጫ ለመምጣት ያስቸግራልና ከፍተኛ ጥንቃቄ አደርግ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ውጤታማ መሆን የቻልኩት” በማለት ተሞክሮውን አጋርቶናል፡፡

ግቢ ጉባኤን በተመለከተ ሲገልጽም “በግቢ ጉባኤ ውስጥ መቆየቴ አንዱ የውጤታማነቴ ምሥጢር ነው፡፡ በግቢ ጉባኤ ያገኘሁት ትምህርት በመንፈሳዊ ሕይወቴም ብቻ ሳይሆን ዓለም ውጣ እንዳታስቀረኝ ትልቅ ትጥቅ ሆኖኛል፡፡ የሚገጥሙኝን ፈተናዎች ለመወጣትና ራሴም በትክክለኛው መንገድ መራመድ እንድችል ትልቅ አቅም ፈጥሮልኛል፡፡ ግቢ ጉባኤ ባይኖርና ወደ ቤተ ክርስቲያን ባንመላለስ ኖሮ በዓለም ጠፍተን እንቀር ነበር፡፡ በግቢ ጉባኤ መታቀፋችን ዋጋው ብዙ ነው” ብሏል፡፡

በዩኒቨርሲቲ ውስጥ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ለሚገኙ ወንድሞችና እኅቶች ባስተላለፈው መልእክትም “ዋናው ዩኒቨርሲቲ ገብቻለሁ ማለት ሳይሆን ለትምህርታቸው ልዩ ትኩረት መስጠት አለባቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውም እየበረቱ እግዚአብሔር እንዲያግዛቸው ራሳቸውን ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጋር ማቆራኘት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ነገ ነገ እያሉ መዘናጋት ብዙ ዋጋ ስለሚያስከፍል የውሳኔ ሰው መሆን፣ ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ያለው ሕይወት ለውጤት እንደማያበቃ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ፈተና ቢገጥም እንኳን እግዚአብሔር ፈተናውን አሳልፎ እንደሚያሻግር መረዳት መልካም ነው፡፡ ይህን ካደረግን እግዚአብሔር አብዝቶ ይባርከናል” ሲል ምክሩን ለግሷል፡፡

የተከበራችሁ የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ድረ ገጽ ተከታታዮች በክፍል ሦስት ዝግጅታችን ደግሞ ከሌሎች ውጤታማ ተመራቂዎች ጋር ያደረግነውን ቆይታ ይዘን እንቀርባለን፡፡ ይቆየን፡፡

ቆይታ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተመራቂዎች ጋር

ክፍል አንድ

በእንዳለ ደምስስ

ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ካለፉት ሠላሳ አንድ ዓመታት ጀምሮ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ በተሰጠው ኃላፊነት መሠረት በሀገር ውስጥ እና በውጪ ሀገራት የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በማስተማርና በማስመረቅ የድርሻውን በመወጣት ላይ ይገኛል፡፡ ወደፊትም ይህንን ኃላፊነቱን ለመወጣት ዘመኑ የዋጀ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቶችን በመስጠት ተመራቂዎች ሀገራቸውንና ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ እንዲሆኑ በትጋት ይሠራል፡፡ በየዓመቱም በርካቶች በተማሩት ትምህርት ውጤታማ ሆነው ዋንጫና ሜዳልያ ተሻላሚዎች ሆነዋል፡፡ “ለዚህ ውጤት እንድንበቃ ማኅበረ ቅዱሳን ትልቁን ድርሻ ይወስዳል” በማለት ዋንጫና ሜዳልያቸውንም ለማኅበሩ ሲያበረክቱ መመልከት የተለመደ ሆኗል፡፡

በ፳፻፲፭ ዓ.ም የቤተ ክርስቲያንና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርታቸውን አጠናቀው ከተመረቁት ውስጥ በርካቶች የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚዎች ሆነዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን ስለ ቆይታቸውና ስለ ውጤታማነታቸው አነጋግረናቸዋል ቀጥለን እናቀርብላችኋለን፡፡

“እግዚአብሔር የክብሩ መገለጫ እንደሚያደርገኝ አልተጠራጠርኩም” (ውብነሽ ለማ)

ውብነሽ ለማ ከ፳፻፲፭ ዓ.ም የግቢ ጉባኤያት ፍሬዎች መካከል አንዷ ናት፡፡ ከቦንጋ ዩኒቨርሲቲ በመካኒካል ኢንጅነሪኒንግ ትምህርት ክፍል ሦስት ነጥብ ዘጠኝ ዘጠኝ (3.99) አጠቃላይ ውጤት በማምጣት የዩኒቨርሲቲው ዋንጫ እና ሁለት ሜዳልያዎች ተሸላሚ ለመሆን በቅታለች፡፡

ዝግጅት ክፍላችንም ስለ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም እና ግቢ ጉባኤ ቆይታዋ አነጋግረናታል፡፡

ውብነሽ ቆይታዋን ስትገልጽ “ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ተመድቤ ስሄድ ቦታው ገና አዲስ ስለ ነበር ፍርሃትና ግራ መጋባትም ገጥሞኝ ነበር፡፡ ነገር ግን ዓላማዬን ለማሳካት ምን ማድረግ አለብኝ ለሚለውና በኅሊናዬ ለሚመላለሰው ጥያቄ መልስ የሆነኝ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መኖርን ነው፡፡ እንደ ዓላማም አድርጌ የገባሁት ራሴን ውጤታማ ሆኜ መውጣትን ነው፡፡ እግዚአብሔር የክብሩ መገለጫም እንደሚያደርገኝ አልተጠራጠርኩም፡፡ ለዚህም መሸሸጊያ ያደረግሁት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ነው፡፡ ቦንጋ ስደርስም በአቅራቢያው ወደ ሚገኘው ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ነው የሄድኩት፡፡” በማለት ትውስታዋን አጋርታናለች፡፡

ጊዜ አጠቃቀሟን በተመለከተ ስትገልጽም፡- “ጊዜዬን በትምህርቴ፣ በጥናቴና በቤተ ክርስቲያን እንዲወሰን ማድረግ ቻልኩ፡፡ ቀድሞም በአካባቢዬ ባለው ቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ አገለግል ስለነበር ሕይወቴን ከቤተ ክርስቲያን ጋር ማቆራኘት አልከበደኝም፤ ሌላም የሕይወት ተሞክሮ አልነበረኝም፡፡ በቅድመ ግቢ ጉባኤም ሆነ በዩኒቨርሲቲው ማኅበረ ቅዱሳን በሚሰጠው የግቢ ጉባኤ አገልግሎት ስሳተፍ ቆይቻለሁ፡፡ ወደ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት በሰንበት ትምህርት ቤታችን ስንሸኝም የተመከርነው ምክር ስንቅ ሆኖኛል” ብላለች፡፡  

ጊዜዋን በአግባቡ መወጣት እንዳለባት ራሷን በማሳመን በዕቅድ በመመራት በተግባርም እንደፈጸመችው የምትገልጸው ውብነሽ ስለ ጊዜ እንዲህ ትላለች፡፡ “ጊዜን በተመለከተ ከቤተሰብ እንደመለየታችን መጠን በራሳችን ላይ የምንወስነው እኛው ብቻ ስለሆንን ነጻነት ይሰማናል፡፡ ብዙዎችም ለመዝናናትና ለማይጠቅሙ ነገሮች ጊዜያቸውን ስለሚያባክኑ ውጤታቸው ላይ ደካማ ሆነው ይገኛሉ፡፡ እኔ ግን ከትምህርቴ በኋላ ከቀኑ ፲ ሰዓት ጀምሮ የምገኘው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው፡፡ አጋጣሚ አስቸኳይ ነገር ሲገጥመኝ ግን በሌሊቱ ቤተ ክርስቲያን ተሳልሜ እመለሳለሁ፡፡ በነበረኝ ቆይታዬም ቤተ ክርስቲያን ሳልደርስ የቀረሁበት ጊዜ የለም፡፡ ከቤተ ክርስቲያን የተለየ ሕይወት ስለሌለኝ መብቴ ብቻ ሳይሆን ግዴታዬም አድርጌ ነው የቆየሁት፡፡ ከትምህርቴ፣ ከጥናት እና ከቤተ ክርስቲያን ውጪ የማሳልፈው ጊዜ ኖሮኝ አያውቅም፡፡

ስለ ጓደኛ ተጽእኖ ላቀረብንላት ጥያቄም “በአጋጣሚ ዓላማችን ተመሳሳይ የነበረ ዐራት ኦርቶዶክሳውያን ወንድሞችና እኅቶች ነበርን የተገናኘነው፡፡ በጣም ደስ የሚል ቅርበት ስለነበረን እንደጋገፋለን፣ አንዱ የሚያውቀውን ለሌላው ለማካፈል አይሰስትም፡፡ በጓደኛ ደረጃ ተሳክቶልኛል ማለት እችላለሁ፡፡ ያም ሆኖ ችግሮች አልነበሩም ማለት አይደለም፡፡ በተለይ የመጀመሪያ ዓመት ላይ በርካታ ዓይኖች ይፈትኑኝ ነበር፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ቸርነት ሁሉን አለፍኩት፡፡ ለዚህም ራሴን በሦስት ነገሮች መጥመዴ ጠቅሞኛል፡፡ በትምህርቴ፣ በቤተ ክርስቲያን(ግቢ ጉባኤ) እና ጥናቴ፡፡

በመማር ላይ ላሉና ወደፊት ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚገቡ ተማሪዎች ባስተላለፈችው መልእክትም “ዓላማቸውን መዘንጋት የለባቸውም፡፡ በኦርቶዶክሳዊነታቸውና በውጤታማነታቸው ከራሳቸው አልፈው የቤተሰቦቻቸው እና የቤተ ክርስቲያን ኩራት እንደሚሆኑ መገንዘብ አለባቸው፡፡ ማንኛውንም አስቸጋሪም ይሁን መልካም የሕይወት ውጣ ውረድ ቢገጥማቸው መሸሸጊያቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንደሆነች ማሰብ፣ በሯን ከፍታም እንደምትቀበላቸው አምነው መጠለል ይገባቸዋል፡፡ ክርስቲያን ከቤተ ክርስቲያን ውጪ ምን ሕይወት አለው? ስለዚህ ተስፋ በመቁረጥ እንዳይዘናጉ፣ ከግል ጥረት ጋር እግዚአብሔርን መመኪያ አድርጎ መጓዝ ይጠበቅባቸዋል” በማለት ከተሞክሮዋ አካፍላናለች፡፡

በቀጣይ በክፍል ሁለት ዝግጅታችን ደግሞ የሌሎችን ኦርቶድክሳውያን ውጤታማ ተመራቂዎች ተሞክሮዎችን ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡ ይቆየን፡፡

የአዲስ አበባ ማእከል በግቢ ጉባኤያት ያስተማራቸውን ተማሪዎች አስመረቀ

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ከመደበኛ ትምህርታቸው በተጨማሪ የቅድሰት ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ትምህርት ተከታትለው ያጠናቀቁ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፮፻ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ሐምሌ ፲፬ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽርሐ ተዋሕዶ አዳራሽ በድምቀት አስመረቀ፡፡

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል የተጀመረ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳንን በመወከል ከሥራ አመራር ጀምሮ በልዩ ልዩ ማስተባበሪያዎች ለረጅም ዓመታት በማገልግል የሚታወቁት በአሁኑ ወቅት የሕብረት ባንክ ም/ፕሬዚዳንት የሆኑት በኩረ ትጕሃን አንዱዓለም ኃይሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ በመልእክታቸውም፡- “መመረቃችሁ አዲስ የሕይወት ምዕራፍ የምትጀምሩበትና ሥራ ለመቀጠርና በጋራ ሆናችሁ ሥራ የምትፈጥሩበት ጊዜ ላይ ደርሳችኋል፡፡ የምታገኟቸውን ዕድሎች መጠቀም፣ ራሳችሁን ማሳደግና በሙያችሁ ብቃት ያላችሁ (  Profesional) ሁኑ፤ ከሁሉም በላይ ግን ፈቃደ እግዚአብሔርን አስቀድሙ” በማለት ከሕይወት ተሞክሯቸው ተነሥተው ለተመራቂዎች ምክርና መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ አካል ከነበሩት ውስጥ አንዱ የዕለቱ ትምህርት ወንጌል ሲሆን በመ/ር ኢዮብ ይመኑ “ሌላ ሸክም አላሸክማችሁም፤ ነገር ግን እስክመጣ ድረስ ያላችሁን ጠብቁ” (ራእ.፪፥፳፭) በሚል ርእስ ለተመራቂዎች ለወደፊት ሕይታቸው ሥንቅና መመሪያ የሚሆን ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አባባ ማእከል ጸሐፊ የሆኑት አቶ ካሣሁን ኃይሌ በኩላቸው ባስተላለፉት መልእክትም “በየጊዜው ማኅበራችሁ ማኅበረ ቅዱሳን እናንተን በማስተማር፣ በመምከር፣ የሕይወት አቅጣጫዎችን በመጠቆም፤ የታተሙ መጻሕፍትን እና ጽሑፎችን በማዳረስ መንፈሳዊ ምግብ እንድትመገቡ ሲያደርግ ቆይቷል፤ እንዲሁም በመደበኛው ትምህርታችሁ እንድትበረቱ ሐሳብ በመስጠት፣ በመደገፍ ንስሓ ገብታችሁ የምሥጢራት ተካፋይ እንድትሆኑ በማድረግ በሕይወታችሁ ላይ ለውጥ አምጥታችኋል” ብለዋል፡፡

አቶ ካሳሁን ከተመራቂዎች የሚጠበቅባቸውን ሲገልጹም “በምትሄዱበት ሁሉ በመንፈሳዊ ሕይወት ራሳችሁን እያነጻችሁ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ባስታጠቀቻችሁ መንፈሳዊ ትጥቅ ሌሎችን በማጽናት በተለይም በልዩ ልዩ ጭንቀት ውስጥ ያለውንና መድረሻ አጥቶ የሚባዝነውን ትውልድ ትታደጉ ዘንድ መትጋት ይጠበቅባችኋል፡፡” ሲሉ የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በተመራቂዎች የቀረቡት የበገናና እና የያሬዳዊ ወረብ፣ እንዲሁም የልዩ ፍላጎት ተመራቂዎች ያቀረቧቸው መንፈሳዊ ዝማሬዎች የመርሐ ግብሩ ልዩ ድምቀት ነበሩ፡፡ በምረቃ መርሐ ግብሩም ላይ ተመራቂዎች፣ የተመራቂ ቤተሰቦች፣ የማኅበረ ቅዱሳን ማስተባበሪያ ኃላፊዎች፣ የግቢ ጉባኤያት መምህራንና የተመራቂዎቹ የንስሓ አባቶች የተገኙ ሲሆን ለተመራቂዎች የአደራ መስቀል በካህናት አባቶች ተባርኮ ተበርክቶላቸዋል፡፡

«ታገኙ ዘንድ ሩጡ» (፩ኛቆሮ.፱፥፳፬)

በመ/ር ተርቢኖስ ቶሎሳ 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በግሪክ ከነበሩ አውራጃዎች አንዷ ከሆነችው አካይያ መዲና ቆሮንቶስ ከተማ ገብቶ ለሕዝቡ ጌታ ከፅንሰቱ ጀምሮ ያደረገውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ ቢነግራቸው ብዙዎቹ ከጣዖት አምልኮ እግዚአብሔርን ወደ ማምለክ፣ ኃጢአትን ከመሥራት ጽድቅን ወደ ማድረግ ተመለሰው፤ አምነው ተጠመቁ፡፡ (ሐዋ.፲፰፥፩–፲)

ቅዱስ ጳውሎስ የቆሮንቶስ ከተማን ሕዝብ አስተምሮ፣ አሳምኖና አጥምቆ ካቆረባቸው በኋላ ከዚያ ወጥቶ ወደ ኤፌሶን ሄደ፡፡ ነገር ግን በቆሮንቶስ ያሉ ምእመናን «አስተምሮ ዋጋ ይቀበላል (ገንዘብ ይበላል)» ብለው አሙት፡፡ ይህንን ሐሜታቸውን ሰምቶ ተስፋ ሳይቆርጥ የወንጌል አገልግሎቱን፣ ማለትም መንፈሳዊውን ትምህርት በሰፊው ቀጥሎበት ለቁመተ ሥጋ ያህል በምእመናን ገንዘብ መመገብ ምንም ቁም ነገር እንዳልሆነ፣ ምንም ሥጋዊ ጥቅም እንደማይፈልግና ገንዘብም እንዳልተቀበላቸው በትምህርቱ ውስጥ ይገልጥ ነበር፡፡ ይልቁንም ቅዱስ ጳውሎስ ይተጋ የነበረው ወንጌልን ስለማስተማር፣ ሰዎችንም ለድኅነት ለማብቃት እንደ ሕጋቸው፣ እንደ አኗኗራቸው ሁሉ እየኖረ ወንጌልን በመስበክ በዓለም በሚደረግ ሰልፍ፣ ሩጫና ሽልማት እየመሰለ ከክርስትና የሚገኘውን ክብር አስተምሯቸዋል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ «በእሽቅድምድም ሥፍራ የሚሽቀዳደሙ ሁሉ እንደሚፋጠኑ አታውቁምን? ለቀደመው የሚደረግለት ዋጋ አለ፤ እንዲሁ እናንተም እንድታገኙ ፈጽማችሁ ሩጡ» ይላል፡፡ (፩ኛቆሮ. ፱፥፳፬) በጦር ሜዳ ተሰልፎ እየፎከረ፣ ጠላቱን ድል የሚያደርግ አርበኛ (ጦረኛ) ከጌታው ዘንድ ሹመት፣ ሽልማት እንዲያገኝ እንዲሁ መንፈሳዊ አርበኛ የሚሆኑ ምእመናንም በምግባር በትሩፋት እየተሸቀዳደሙ ዋጋቸውን (ክብራቸውን) ያገኙ ዘንድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አጥብቆ ይመክራቸዋል፡፡

መሮጥና ማግኘት የሚሉትን ፀንሰ ሐሳቦች ሐሳብ በሁለት መንገድ ማየት እንችላለን፡፡ አንደኛው፡- በዚህ ዓለም በሚደረግ የሩጫ ውድድር አንጻር በክርስትና የሚደረግ የሕይወት ዕድገትና መንፈሳዊ ፉክርክር ነው፡፡ አትሌቶች ሀገራቸውን ወክለው በሩጫ ተወዳድረው አሸናፊ ሆነው ተሸልመው የራሳቸውንም የሀገራቸውንም ስም በዓለም ያስጠራሉ፤ ሥጋውያን ሯጮጭም ሲሮጡ በመንገዳቸው ላይ የሚደርስባቸውን ድካም የሚገጥማቸውንም መሰናክል ተቋቁመው የሚያልፉትና ለአሸናፊነት የሚበቁት በአሸናፊነታቸው የሚያገኙትን ክብርና ሽልማት ተስፋ በማድረግ ነው፡፡ ይህንንም ተስፋ ሳይጠራጠሩ እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት ይሮጣሉ፡፡

መንፈሳውያን ሯጮች የሆኑ ምእመናንም እንዲሁ በኅሊናቸው ከዚህ ዓለም ድካምና ፃዕር በኋላ ያለውን የዘለዓለም ሕይወትና የማያልፍ ተድላ ደስታን እያሰቡ ወደ መንግሥተ ሰማያት በእግረ ኃሊናቸው በጽናት ይሮጣሉ፡፡ በሕይወት መንገዳቸው ላይ ከፈቃደ ሥጋቸው፣ ከአጋንንትና ከዐላውያን ነገሥታት ሁሉ የሚደርስባቸውን የቅድስና ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ሩጫ መሰናክሎችን በፍጹም እምነትና በጽናት አሸንፈው በእግዚአብሔር ዘንድ የዘለዓለማዊው ሕይወት የመንግሥተ ሰማያት ተሸላሚ ይሆናሉ፡፡

ክርስቲያን ሁል ጊዜም በምግባረ ክርስትና የሚሮጥ (የሚያድግ) ነው፤ ምግባረ ክርስትና እግዚአብሔርን የምንመስልበት ሕይወት ነው፡፡ ሐዋርያው «እኔ ክርስቶስን እንድመስለው እናንተም እኔን ምሰሉ» እንዳለ፡፡ (፪ኛቆሮ.፲፩፥፩) በጥንተ ፍጥረትም አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር «ሰውን በአርአያችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠር>> ብሎ እርሱን የመምሰል ሕይወት በሰው እንደሚገለጥ ተናግሯል፡፡ (ዘፍ.፩፥፳፮) እግዚአብሔር ደግሞ በባሕርዩ መልካም ነው፤ ለመልካምነቱም ገደብ የለውም፡፡

ምግባረ ክርስትና ገደብ የለውም፤ ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡ እስከ አሁን የጾምኩት፣ የጸለይሁት፣ ያስቀደስኩት፣ የቈረብኩት ይበቃኛል፣ … አይባልም፡፡ ምክንያቱም የምንነሣበት እንጂ የምንደረስበት ምግባር የለምና፣ በጎነት መጨረሻ የለውም፡፡ ስለዚህ የክርስቲያን ኑሮው ሁል ጊዜ በሩጫ (በበጎ ምግባር መገሥገሥ) ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ «በኋላዬ ያለውን እየረሳሁ በፊቴ ያለውን ለመያዝ እጄን እዘረጋለሁ» ያለውም ለዚህ ነው፡፡ (ፊል.፫፥፲፫) ተክል እንደተተከለ ብቻ ከቀረ ይደርቃል እንጂ አያድግም፡፡ ስለዚህ አድጎ ፍሬ እንዲያፈራ ይኮተኮታል፤ ከአፈር፣ ከአየር እና ከውኃ ይመገባል፡፡  ከዚህም የተነሣ አድጎ፣ ለምልሞና አብቦ ያፈራል፤ ክርስቲያናዊ ሰውም እንዲሁ ነው፡፡ በሃይማኖትና በጥምቀት፣ ይተከላል፤ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይመገባል፤ በምግባር ለምልሞ፣ በትሩፋት አብቦ የክብር ፍሬ ያፈራል፡፡ ስለዚህ በክርስትና ሁል ጊዜም ማደግ ነው፡፡

በክርስትና ሕይወት ውስጥ ምግባር ሃይማኖት «እዚህ ጋር ይበቃኛል» ብለን የምናቆመው ሳይሆን ዕለት ዕለት መሽቀዳደም፣ ለፍቅር፣ ለየዋሀት፣ ለቅንነት፣ ለለጋሥነት፣ ለርኅራኄ … መፎካከር ነው፡፡ ሐዋርያው «ፍቅርን ተከተሏት>» በማለት እንዳስተማረን፡፡ (፩ኛቆሮ.፲፬፥፩) እንዲህ ከሆነ በሰማይ የሚገኘው ክብር ታላቅ ነው፡፡ ክብር ሁሉ በሥራ መጠን ነውና ለሁሉም እንደ ዋጋው እከፍለዋለሁ እንዳለው አምላካችን ጥቂት የሠራ ጥቂት ክብር ይቀበላል፤ አብዝቶ የሠራም አብዝቶ ይቀበላልና፡፡ (ራእ.፳፪፥፲፪)

ሁለተኛው በጦር ሰልፍ በሚደረግ ሩጫ አንጻር በተጋድሎ የሚገኝ ጸጋን ለማመልከት ነው፡፡ ከላይ እንዳየነው የጦር ሰልፍ ሩጫ ጠላትን ድል አድርጎ ነፃነትን ማወጅ፣ ከድል በኋላ የሚገኝን ሹመትንና ሽልማትን ገንዘብ ማድረግ፣ ክብርንና አዎንታዊ የታሪክ ባለቤት መሆንን መቀዳጀት ነው፡፡ ስለዚህ ሥጋውያን ጦረኞች እግራቸውን ለጠጠር፣ ግንባራቸውን ለጦር ሰጥተው ከድል በኋላ ስለሚያገኙት ሽልማት እኔ ልዝመት እኔ ልዝመት ብለው ይሽቀዳደማሉ፡፡

ከተጋድሎ በኋላ የሚያገኘውን ክብር የሚያስብ ክርስቲያንም እንደዚሁ ዲያብሎስ ያሰለፈውን ጦር ድል ለመንሣት ይሰለፋል፣ ሞትንም አይፈራም፡፡ «ብእሲ ዘይሬኢ አክሊላቲሁ ኢይሜምእ፤ አክሊሉን የሚያይ ሰው ወደ ኋላ አያፈገፍግም» በማለት እንዳስተማረን፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ተግሣጽ) ከፊቱ የሚጠብቀውን ክብርና ሽልማት የሚያስብ ተጋዳይ በአሁናዊ መከራው አይማረርም፡፡ መዝሙረኛው ዳዊት እንዲህ ይላል «እለ ይዘርዑ በአንብዕ ወበሐሴት የዐርሩ፤ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ ወጾሩ ዘርዖሙ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ ወጾሩ ከላስስቲሆሙ፤ በልቅሶ(በዕንባ) የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ፤ በሄዱጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዷቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ» እንዲል፡፡ (መዝ.፻፳፭፥፮-፰)

በክረምት የሚዘራ ገበሬ ጠዋት ሲወጣ በላይ ዝናቡ ይወርድበታል፤ በታች ቅዝቃዜው፣ ጭቃውና ጎርፉ ይፈራረቁበታል፤ ስለዚህ በመከራ ይዘራል፡፡ የዘራው አፍርቶ አጭዶ ሲከምረው ግን መከራውን ረስቶ ጨምሬ ዘርቼ ቢሆን ኖሮ ይላል፤ እሸቱን እየበላ ነዶውን ሲሰበስብም ደስ ይለዋል፡፡ እንዲሁ በክርስትና ሕይወታቸው የጸኑ ሰማዕታት ከተሳለ ስለት፣ ከነደደ እሳት ሲገቡ መከራው ይሰማቸዋል፤ ጻድቃን ፍትወታት እኩያት ኃጣውእ ርኵሳት ሕሊናቸውን ያስጨንቃቸዋል፣ ድል ከነሡ በኋላ ግን ሰማያዊ አክሊልን ተቀዳጅተው በተድላ በደስታ ይኖራሉ፡፡

ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ በአካለ ነፍስ ሆኖ መነኮሳት በአክናፈ እሳት ወደ ኢየሩሳሌም ሲገቡ አይቶ አንድን አባት «ሰላም ለክሙ ብፁዓን መነኮሳት፤ ንዑዳን ክቡራን መነኮሳት ሆይ ሰላም ለእናንተ ይሁን»  አለው፡፡ መነኮሱም «አንተም እንጂ ንዑድ ክቡር ነህ በዘመንህ ቀርነ ሃይማኖት ቆሞልሀልና» አለው፡፡ ቆስጠንጢኖስም «ይህንን አውቄስ ቢሆን መንግሥቴን ትቼ እንደ እናንተ በምናኔ በኖርሁ ነበር» ብሎታል፡፡ (ፊልክስዩስ) ስለዚህ የዚህን ዓለም መከራና ሥቃይ የወዲያኛውን ክብር ያስረሳዋል፡፡ በዚህ ዓለም ሴት ልጅ በጭንቅና በምጥ ስትወልድ ታዝናለች ከወለደች በኋላ ግን ደስ ይላታል፤ ከወደለች በኋላ ግን ጭንቋንና ምጧን አታስበውም፤ ምክንያቱም ጨንቋንና ምጧን በልጇ ስለምትረሳው፡፡ (ዮሐ.፲፮፥፳፩) ስለዚህ ክርስቲያኖችም የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ በተጋድሎና በትዕግሥት ሊያልፉት ይገባል፡፡ እንዲህም ከሆነ በሰው ኅሊና የማይተረጎም ሰማያዊ ክብርን ያገኛሉ፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ «እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወት አክሊልንም እሰጥሀለሁ» እንዲል፡፡ (ራእ.፫፥፲) ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት በተጋድሏቸውና በአሸናፊነታቸው ከሚቀበሉት ክብር አንጻር አሁን የሚያገኛቸው መከራ ኢምንት ነው፡፡ ስለዚህ ሰማያዊውን ክብር ለማግኘት መንፈሳዊውን ሩጫ መሮጥ ከኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፣ ወለወላዲቱ ድንግል፣ ወለመስቀሉ ክቡር፡፡