የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የአዲስ ዓመት ቃለ በረከት

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ዐሠርቱ ወአምስቱ ዓመተ ምሕረት፡-

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

-በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣

-ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣

-የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣

-በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤

-እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤት የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵውያት በሙሉ!

የዓመታትና የአዝማናት ባለቤት የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለአዲሱ ዓመት ለሁለት ሺሕ ዐሥራ አምስት ዓመተ ምሕረት ዘመነ ሉቃስ በሰላም አደረሳችሁ !!

ወዓመቲከኒ ለትውልደ ትውልድ፤ ዓመቶችህ ለልጅ ልጅ ናቸው (መዝ. ፻፩፥፳፬)፡፡

ይህንን ቃለ እግዚአብሔር የተናገረው እግዚአብሔር በቅብዕ ቅዱስ አማካኝነት ሀብተ ትንቢት ወመዝሙር ያሳደረበት ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ነው፤ የቃሉ መሠረተ ሐሳብም ዓመታት የእግዚአብሔር ስጦታ መሆናቸውን፣ እንደዚሁም የተሰጡት ለሰው ልጆች መሆናቸውን ይገልፃል፡፡ በእርግጥም ዓመታት ከእግዚአብሔር ለሰው ልጆች የተሰጡ ሀብቶች ናቸው፤ ዓመታት፣ ወራት፣ ዕለታት፣ ቀናት፣ ሰዓታት የሚያስፈልጉት ለሰው ልጅ እንጂ ለእግዚአብሔርና በመንፈሳዊ ዓለም ለሚገኙ ፍጡራን አይደለም፡፡ ምክንያቱም ሰው በደካማው ዓለም የሚኖር ደካማ ፍጡር ስለሆነ ለኑሮው ጊዜያት የግድ ያስፈልጉታል፤ በመንፈሳዊ ዓለም የሚገኙ ፍጡራን ግን፣ ድካም የሌለባቸው ትጉሃን ስለሆኑ፣ ዓመትም ቀንም ሰዓትም ወዘተ አያስፈልጋቸውም፤ የሰዓት መለኪያ ብርሃንም የላቸውም፤ ምክንያቱም ያሉበት ዓለም ሁሌም ብርሃን እንጂ ጨለማ ስለማይፈራረቀው፣ እንደዚሁም ተለዋዋጭ አየርም ሆነ ዕድሜ ስለሌላቸው ማለት ነው፡፡ ለሰው ግን የጊዜ መለኪያ የሚሆኑ ብርሃናትና አዝማናት ወዘተ የተመደቡለት ስለሆነ፣ በእነሱ እየተመራ ጊዜያትን ይለካል፤ ዓመታትን ወራትንና ቀናትን ወዘተ ይቈጥራል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፡

ዓመታት ከእግዚአብሔር ለእኛ የተሰጡን ያለ ምክንያት አይደለም፤ የእግዚአብሔር ስጦታ ሁሉ ክብርም ጥቅምም አለውና ልናከብረውና ልንጠቀምበት እንጂ፤ ሁላችንም እንደምንገነዘበው ጊዜ ትልቁና ቀዳሚው የሥራ መሣሪያ ነው፡፡ እህልን ዘርተን የዓመት ምግባችንን የምናገኘው ወርኃ ክረምት ስለተሰጠን ነው፤ ይህ ወቅት ባይኖር ኖሮ የእርሻ ሥራ ሠርተን ራሳችንን መመገብ እንደማንችል የምንስተው አይሆንም፡፡ ከዚህ አንጻር ዓመታትንና ወቅቶችን እንደ አመቺነታቸው እየተጠቀምን ልንሠራባቸው እግዚአብሔር አመቻችቶ ሰጥቶናል ማለት ነው፤ ስለዚህ በብሂለ አበው “ጊዜ ሳለ ሩጥ ….” እንደሚባለው ሁሉንም በጊዜው ጊዜ መሥራትና ተጠቃሚ መሆን ያስፈልጋል፡፡ ሰውም ሆነ ጊዜ ለሥራ የተፈጠሩበት ምክንያት መክበርም መዳንም ማግኘትም ማደግም መልማትም በሥራና በሥራ ብቻ የሚገኝ ከመሆኑ የተነሣ እንደሆነ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፤ “ብላዕ በሐፈ ገጽከ፤ በፊትህ ላብ እንጀራህን ብላ” የሚለው አምላካዊ ትእዛዝም ይህንን ይገልጻል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፡

እግዚአብሔር አምላክ ያለመታከት ሠርተን ራሳችንን በራሳችን የምናስተዳድርባት በሀብትና በጊዜ የተዋበች ምድር አስረክቦናል፤ ምድሪቱንም ለእኛ በሚመች አኳኋን አበጅተን እንድንጠቀምባት የሚያስችል አእምሮና ጉልበትም ከጤና ጋር ሰጥቶናል፤ ሐቁ ይህ ከሆነ ታድያ ለምንድን ነው በምድራችን ስጋትና ጭንቀት፤ ረኃብና እርዛት፣ የሀብት እጥረትና የእርስ በርስ ግጭት በስፋት የሚታየው የሚለውን ጥያቄ ሰው ሁሉ በጥልቀት ሊያጤነው ይገባል፡፡ እግዚአብሔር የሰጠን ምድር አሁንም ለፍጡራን የሚበቃ የተትረፈረፈ ሀብት ያለ ጥርጥር አላት፣ የአጠቃቀም ጉዳይ ካልሆነ በቀር ሀብት የሌለው የምድር አካባቢ ፈጽሞ የለም፡፡ ይህም ከሆነ ሁሉም ወደ ሥራና ሥራ ብቻ ተሠማርቶ ጥረቱን ከቀጠለ የሚያጣው ነገር የለም ማለት ነው፡፡ ሰው ጤና ዕውቀትና ሰላም ካለው ሀብታም ነው፤ ምክንያቱም እነዚህ ከተሟሉለት ሌላው ሁሉ እግዚአብሔር ከሰጠው ምድር ሠርቶ የሚያገኘው ነው፡፡ ሰላም ከሌለ ግን ነገሩ ሁሉ ጨለማ ይሆንበታል፤ አካላዊና አእምሮአዊ ጤናውም ይደፈርስና ሳያጣ ያጣ ወደ መሆን ይቀየራል፡፡ ዛሬ በሀገራችንም ሆነ በዓለማችን እየተከሠተ ያለው ሐቅ ይኸው ነው፡፡ ይህ የሰላም እጦት በሀገራችን በኢትዮጵያ በርከት ላሉ ዓመታት እየተደጋገመ በመከሠቱ፣ በዚህ ጠንቅ ሕዝባችን ሳያጣ ያጣ ሆኖአል፤ ኢትዮጵያን በመሰለች ለምና ምድራዊት ገነት ተቀምጠን፣ በዓለም ውስጥ የድህነት ተምሳሌት ሆነን መገኘታችን፣ የሁላችንም ኅሊና ሊኰረኲረው ይገባል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፡-

በአዲሱ ዓመት ለኢትዮጵያውያን ልጆቻችንና ወገኖቻችን ሁሉ በአጽንዖት የምንመክረው ዓቢይ ምክር በግጭት ችግሮቻችንን መፍታት በፍጹም አንችልም፤ በመራራቅም ማደግ አንችልም፤ በተለያየን ቊጥር ድህነታችንን ከማስቀጠልና ደካሞች ከመሆን በቀር የምናገኘው አንዳች ፋይዳ የለም፤ እውነቱ ይህ ከሆነ ከገባንበት ያላስፈላጊ ግጭት በፍጥነት ወጥተን ዘላቂ መፍትሔ ማምጣት ወደሚያስችል ወደ ምክክርና ውይይት እንግባ፤ አዲሱ ዓመት እውነተኛ አዲስ ዓመት ሊሆን የሚችለው ይህንን ያደረግን እንደሆነ ነው፡፡ አሮጌውን አስተሳሰብ እንዳለ ተሸክመን ለመቀጠል እየዳዳን ከሆነ አዲስ ዓመት ማለቱ የአፍና የጆሮ ቀለብ ከመሆን በቀር የሚሰጠን አንዳች ትርጉም የለም፡፡ ስለሆነም አዲሱን ዓመት አዲስ የሆነ የሰላምና የዕርቅ የስምምነትና የአንድነት የይቅርታና የምሕረት የፍትሕና የእኩልነት መርሕ አንግበን ፍጹም ሰላምን ለማንገሥ በቊርጥ ማሰብና መነሣሣት አለብን፣ ይህንንም ለማሳካት በአንድ አዳራሽ፣ በአንድ ጠረጴዛ ተገናኝተን ችግሮቻችንን በውይይትና በምክክር እንድንፈታ በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም፡-

አዲሱ ዓመት የሰላም የፍቅር የበረከት የዕድገት የሃይማኖትና የልማት ዓመት እንዲሆንልን ወደ እግዚአብሔር በመጸለይና በብሩህ ተስፋ እንድንቀበለው መልእክታችንን በድጋሚ በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር መልካም አዲስ ዓመት ያድርግልን!

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

መስከረም ቀን ፳፻፲፭ ዓመተ ምሕረት

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ፡፡

ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል

በጳጉሜን ወር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በድምቀት ከሚከበሩ በዓላት አንዱ የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ በዓል ነው፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ነው፡፡ “ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ” እንዲል፡፡ (ጦቢ. ፲፪፥፲፭) ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ይህንን መሠረት አድርጋ ጳጉሜን ፫ ቀን በየዓመቱ በዓሉን ታከብራለች፡፡

በዓሉን የምናከብርበት ምክንያት በድርሳነ ሩፋኤል ላይ እንደሚከተለው ተጽፏል:-

ይህም ዕለት በሊቀ ጳጳሱ በአባ ቴዎፍሎስ ዘመን እስክንድርያ በምትባል ሀገር ዳርቻ ባለች ደሴት በውስጧ ብዙ ተአምራት የተፈጸሙባት በቅዱስ ሩፋኤል ስም ያታነጸች ቤተ ክርስቲያን የተባረከችበትና የተቀደሰችበት ዕለት ነው፡፡ ይህም የሆነው አንዲት በጣም ሀብታም የሆነች ሮማዊት ሴት ንዑድ ክቡር የሚሆን የቅዱስ ሩፋኤልን ሥዕልና ልጆቿን እንዲሁም ከባሏ በውርስ ያገኘችውን ብዙ ገንዘብ ይዛ ወደ ሊቀ ጳጳሱ ወደ አባ ቴዎፍሎስ ዘንድ በመጣችበት ጊዜ ነበር፡፡ ከመጣችም በኋላ በሊቀ ጳጳሱ ቤት ፊት ለፊት ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችና ከመሬት ውስጥ ወርቅ የተከማቸበት ሳጥን ተገኘ፡፡

ከዚህም በኋላ ሊቀ ጳጳሱ አባ ቴዎፍሎስ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አሣነጸ፤ ከእነዚህም ውስጥ እስክንድርያ በምትባል ሀገር ዳርቻ ባለች ደሴት ላይ ክቡር በሚሆን በቅዱስ ሩፋኤል ስም የተሠራች ይህች ቤተ ክርስቲያን ትግኝበት ነበር፡፡ ሥራዋንም ሠርቶ በፈጸመ ጊዜ በዚችው ዕለት በታላቅ ክብር አከበራት፣ ባረካት፣ ቀደሳት፡፡ ብዙ ሕዝብና ምእመናን በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ሲጸልዩ ሣለ ቤተ ክርስቲያኒቱ ተንቀጠቀጠች፤ ብዙም ታወከች ማዕበልም እንደሚያንገላታው መርከብ ተንገላታች፡፡ ከመንቀጥቀጡም የተነሣ ቤተ ክርስቲያኒቱ በባሕር አሸዋ ላይ እና ለመንቀሳቀስ በባሕር ውስጥ ጸንቶ የሚኖር ከሌሎች ዓሣ ነባሪዎች እጅግ የሚበልጥ አሣ ነባሪ ጀርባ ላይ የታነጸች መሆኗን ዐይተው ተረዱ፡፡

ያም ዓሣ ነባሪ ከሰዎች ብዛት የተነሣ ክብደት ስለተሰማው ያቺን ቤተ ክርስቲያን ይገለብጣት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፤ በውስጡ ያሉ ሰዎች እና ሊቀ ጳጳሱ ያድናቸው ዘንድ ወደ ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በታላቅ ቃል ጮኹ፡፡ ክቡር የሚሆን ወደ ቅዱስ ሩፋኤልም ማለዱ፡፡

በዚያን ጊዜ ልዑል እግዚአብሔር ንዑድ ክቡር የሚሆን ቅዱስ ሩፋኤልን ላከላቸው፡፡ ከጭንቀታቸውም አዳናቸው፤ ከሐዘናቸውም አረጋጋቸው፣ ዓሣ ነባሪውንም “ባለህበት ቦታ ሳትንቀሳቀስ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ጸንተህ ኑር” በማለት በያዘው ጦር ወግቶ እንዳይንቀሳቀስ ጸጥ አስደረገው፡፡ ያለ ምንም መንቀሳቀስ ባለበት ቦታ ጸጥ ብሎ ቆመ፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በዚያች ቤተ ክርስቲያን ብዙ ድንቅ ተአምራት ሲደረግባት፣ ሕሙማን ከደዌአቸው ሲፈወሱባት ቆዩ፡፡

ነገር ግን የእስላሞች መንግሥት እስኪቋቋም ድረስ በዚያ ሁኔታ እንዳለች ከዕለታት በአንድ ቀን ዓሣ ነባሪው ተንቀሳቀሰና የረጋ ባሕር ማዕበል ሞገድ ተነሥቶ ስለመታው ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈራረሰች፡፡ በዚያች ቦታ ላይም የሚኖሩትን ብዙ ሰዎች ባሕሩ አሰጠማቸው፡፡

የቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ ስለ ቅዱስ ሩፋኤል ታላላቅ ተአምራት ለጻድቁ አኖሬዎስ እንዲህ ሲል ተናገረ፤ “ንጉስ ሆይ እንግዲህ በማስተዋል ስማ ወደ አንተ እንመጣ ዘንድ በመርከብ ተሣፍረን ነበርና እንዲሁ በጉዞ ላይ ሳለን በአንድ ደሴት ውስጥ አንዲት ቤተ ክርስቲያን አየን ቀኑም ቀዳሚት ሰንበት ነበር፡፡ ወደ ወደቡም በደረስን ጊዜ ቅድስትና ክብርት በምትሆን በዕለተ ሰንበተ ክርስቲያን የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ለመቀበል ወደ እርሷ ስናመራ በዚያች ቤተ ክርስቲያን አካባቢ አንዲት አነስተኛ ደብር አገኘን፡፡ በውስጧም የሚኖሩ ብዙ ወንድሞች መነኮሳት ነበሩ፡፡ ክብር ምስጋና ለእርሱ ይሁንና በእግዚአብሔር ትእዛዝ ወደ እነርሱ በደረስን ጊዜ ምናልባት ከቀድሞ አባቶች የተፃፈ መጽሐፈ ብሉይ በእናንተ ዘንድ ቢኖር እመራመርበት ዘንድ ብትሰጡኝ ፈቃዳችሁን እጠይቃለሁ” አልኳቸው፡፡ እነርሱም “በቤተ ክርስቲያኒቱ ግምጃ ቤት ውስጥ ብዙ መጻሕፍት ይገኛሉ፤ ነገር ግን እኛ ትርጉማቸው ምን እንደሚል አናውቅም” አሉኝ፡፡

እኔም እስኪ አምጥታችሁልኝ ልመልከታቸው አልኳቸውና ካመጡልኝ በኋላ በእግዚአብሔር በደቀ መዛሙርት ፊት ያደረጋቸውን ልዩ ልዩ ተአምራትና ስለ ሰማይና ምድር ጥንት ተፈጥሮ እንዲሁም ከፍጥረተ ዓለም እስከ ኅልቀተ ዓለም ድረስ ያሉትን ሁኔታዎች ስመራመር አገኘሁ፡፡ እንዲሁም ሌሎችን መጻሕፍት ስመራመር ደቀ መዛሙርቱ ምሥጢረ መለኮቱን ይገልጥላቸው ዘንድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ጠይቀውት በደብረ ዘይት ሰብስቧቸው ሳለ ስለ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሹመትና ማዕረግ የሚያስረዳ አባቶቻችን ሐዋርያት የጻፉትን አንድ መጽሐፍ አገኘሁ፡፡

በውስጡ የተፃፈውም እንዲህ የሚል ነበር፡፡ ሐዋርያት ፈጣሪያቸውን ጌታችን አምላካችን እግዚአብሔር ሆይ ስለ ቅዱስ ሩፋኤል ክብር ታስረዳን ዘንድ እንለምንሃለን፡፡ በምን ቀን፣ በየትኛው ወር እንደሾምኸው፣ ክብሩና ማዕረጉ፣ ከሌሎቹ ሊቃነ መላእክት ክብር ጋር ትክክል እንደሆነ ስለ እርሱ በዓለሙ ሁሉ እንድናስተምር ትገልጽልን ዘንድ እንማልዳለን አሉት፡፡

እርሱም ከወሩ አነስተኛ በሆነችው በጳጉሜን ሦስት ቀን የመታሰቢውን በዓል አድርጉ ብሎ ስለ አዘዛቸው በዚሁ ዕለት በዓሉ ይከበር ዘንድ ሕግ ሠርተው ወሰኑ፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቍስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ይገልጻሉ፡፡ “በበሽታ ሁሉ ላይ በሰው ልጆችም

ቍስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል (ሄኖክ ፲፥፲፫)፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል ላረገዙ ሴቶችም ረዳታቸው ነው፡፡ ሴት በፀነሰቸወበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያትም፡፡ ጽንሱ በማኅፀን እያለ ተሥዕሎተ መልክዕ (መልኩ በሥላሴ አርአያ መሳል) ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ ቅዱስ ሩፋኤል በጥበቃው አይለያቸውም፡፡ በመውለጃቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማኅፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀልላቸዋል፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል የሰውን ልጆች በምንዝር ጌጥና በመሳሰሉት እንዲያጌጡ እንዲሁም ክፉ ሥራን እንዲሠሩ፣ ከእግዚአብሔርም እንዲለዩ ለማድረግ የሚጥረውን ጋኔን የመገሠጽ እና ያደረባቸውን ክፉ መንፈስ እንዲያስወግድ ሥልጣን የተሰጠው መልአክ ነው፡፡ “አዛዝዓልም ለሰዎች ሰይፍን ሾተል፣ ጋሻና ጥሩር መሥራትን አስተማራቸው፡፡ ከእነርሱም በታች ላሉት አምባሮችን፣ ጌጥን፣ ዐይን መኳልንና ቅንድብ መሸለልን፣ ከተመረጠና ከከበረ ከዕንቍም ሁሉ በከበረውና በተመረጠው ዕንቍ ማጌጥን፣ እንሶስላ መሞቅን ሁሉና የዓለሙን ለውጥ አሳያቸው፡፡” እንዲል (ሄኖክ ፪፥፲፰)፡፡ ይህን አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አሥሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡

የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል በረከት ረድኤት ይደርብን፡፡

ሱባዔያችን በረከት የሚያሰጥ ይሁን

እንኳን ለእመቤታችን የትንሣኤና ዕርገት በዓል በሰላም አደረሳችሁ – አደረሰን፡፡

በእንዳለ ደምስስ

ከነሐሴ አንድ ቀን ጀምሮ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት እናገኝ ዘንድ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከደነገገቻቸው ሰባቱ አጽዋማት መካከል ፍልሰታ ለማርያም ጾምን ስንጾም ቆይተናል፡፡ ከጾሙ ጋር ተያይዞ አንዳንድ ሥርዓት ሊበጅላቸውና “ሳይቃጠል በቅጠል” እንዲሉ አበው ሊስተካከል ይገባል ያልኩትን በሐመር መጽሔት ፳፻፲፩ ዓ.ም መንገደኛው ዓምድ ላይ ያሰፈርሁትን ጽሑፍ ለዛሬ ለድረ ገጹ ቢሆን ብዬ አቅርቤዋለሁ፡፡ መልካም ንባብ፡፡

እንደምን ሰነበታችሁ? መንገደኛው ነኝ፡፡ እነሆ ከእመቤታችን ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም በረከትን በመሻት በፍልሰታ ለማርያም ሱባዔ ለመያዝ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም በታነጸውና በቤተ ክርስቲያናችን ከሚታወቁ ታላላቅ ገዳማት በአንዱ ከዋዜማው ጀምሮ ተገኝቻለሁ፡፡

ለሱባኤ የሚያስፈልጉኝን የጸሎት መጻሕፍትና አልባሳት በቦርሳ አድርጌ በጀርባዬ አዝዬ፣ የጸበል መቅጃ አነስተኛ ጀሪካን፣ ሽንብራና በሶ በፌስታል አንጠልጥዬ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሔጄ ተሳለምኩ፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን እንደ እኔ በረከት ፍለጋ፣ በጾም በጸሎት ተወስነው ከአምላካቸው ከእግዚአብሔር ለመገናኘት፣ የልቦናቸውን መሻት ይፈጽምላቸው ዘንድ ለመማጸን ያለማቋረጥ ወደ ገዳሙ ይጎርፋሉ፡፡

በበጎ አድራጊ ምእመናን እንደታነጹ የሚታወቁት የወንዶችና የሴቶች የሱባዔ መያዣ በአቶች(አዳራሾች) ከቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ውጪ በስተ ምሥራቅና በስተ ምዕራብ ሽንጣቸውን አርዝመው ለመስተንግዶ በራቸውን ከፍተዋል፡፡ በበሮቹ መግቢያና መውጫዎች የሚገቡና የሚወጡ ምእመናን ግርግር አካባቢውን የገበያ ውሎ አስመስሎታል፡፡ ሁሉም ይጣደፋል፡፡ ግርግሩን እየታዘብኩ ለሱባዔ ወደ ገዳሙ መምጣቴን ለማሳወቅና ቦታ እንዲሰጠኝ ለመጠየቅ ወደ አስተናጋጆቹ ሔድኩ፡፡ ማንነቴን የሚገልጽ መታወቂያ በማቅረብ አስመዝግቤ ወደተመደብኩበት የወንዶች አዳራሽ አመራሁ፡፡

ገና ከቀኑ ስምንት ሰዓት ቢሆን ነው፡፡ አዳራሹ በመጋረጃ መሐል ለመሐል ተከፍሎ በርካታ ምእመናን እንዲያስተናግድ ተደርጎ ተዘጋጅቷል፡፡ ወለሉ ሙሉ ለሙሉ ምንጣፍ ተነጥፎበታል፣ ቀድመውኝ የመጡ ምእመናን የራሳቸውን ምንጣፍ፣ ካርቶን፣ ከምንጣፉ በላይ ደርበው አንጥፈዋል፡፡ አብዛኛው የአዳራሹ ሥፍራ ተይዟል፡፡ ቦታ ፍለጋ ዓይኖቼን አንከራተትኳቸው፡፡ ቢያንስ አምስት ሰው ሊያስተናግድ የሚችል ቦታ እንዳለ አስተዋልኩ፡፡ የሚመቸኝን ቦታ ከመረጥኩ በኋላ ጓዜን አስቀምጬ ምንጣፍ ዘረጋሁ፡፡

ራሴን ካረጋጋሁ በኋላ አዳራሹን ከላይ እስከ ታች በዐይኖቼ ቃኘሁት፡፡ አብዛኛው በአዳራሹ ቦታ ይዘው ያሉት ወጣቶች ናቸው፡፡ አልፎ አልፎ ግን በጎልማሳነት ዕድሜ ላይ ያሉ፣ በሕመም ምክንያት በአስታማሚ የሚረዱ ሰዎችም አብረውን አሉ፡፡ ከሁሉም ግን ትኩረቴን የሳበው  በስተቀኝ በኩል ግድግዳውን ተደግፈው ከአንድ ሱባዔ ከሚይዝ ሰው የማይጠበቅ ፌዝና ቀልድ ላይ ያተኮረ የወጣቶቹ ድርጊት ነው፡፡ ገና ከዋዜማው እንዲህ ከሆነ ጥቂት ሲቆይ ለጸሎትም እንኳን እንደምንቸገር መገመት አላዳገተኝም፡፡ እኔም አላርፍም እነሱን መከታታል ጀመርኩ፡፡ እየተቀላለዱ ይሳሳቃሉ፡፡

የልጆቹ ሁኔታ ስላላማረኝ ነጠላዬን መስቀልያ ለብሼ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሔድኩ፡፡ አሁንም የቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር በጸበልተኛና ሱባኤ በሚገቡ ምእመናን ግርግር እንደተሞላ ነው፡፡ ያሰብኩትን ሱባዔ በሰላም አስጀምሮ በሰላም እንዲያስፈጽመኝ ተማጸንኩ፡፡ ጠዋት የጸበል መጠመቂያ ቦታውን በመፈለግ እንዳልደናበር ወደ አንድ ጸበልተኛ ጠጋ ብዬ “ጸበል መጠመቂያው የት ነው?” ብዬ ጠየቅሁት፡፡

በጣቱ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ እያመለከተኝ “በዚህ በኩል ነው፡፡ ቢያንስ አራት ወይም አምስት ደቂቃ ብቻ ቢወስድ ነው” አለኝ፡፡ በደንብ ሲያስተውለኝ እንግዳ መሆኔን በመረዳት “ለመጀመሪያ ጊዜ ነው የመጣኸው?” አለኝ፡፡

“አዎ፡፡” አልኩት፡፡

“ወንድሜ ራስህን በደንብ መጠበቅ አለብህ፡፡ በእግዚአብሔር ወይም በእመቤታችን እንዳታማርር፡፡ የሰው ፍላጎቱ ብዙ ነው፡፡ ለበረከት የሚመጣ እንዳለ ሁሉ ለስርቆትና ለክፉ ነገር የሚመጣም አለ፡፡ ጸበል ስትጠመቅ ያወለቅኸውን ልብስ ይዞብህ፣ ወይም ለብሶብህ የሚሔድም አይጠፋም፡፡ ንብረትህን በደንብ መጠበቅ አለብህ፡፡ እንዲህ ስልህ ለነፍሳቸው ያደሩ፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ያስገዙና ስለሌሎች የሚኖሩ የሉም እያልኩህ አይደለም፡፡ ሥፍራው ታላላቅ ተአምራት የሚከናወንበት የጽድቅ ሥፍራ ነው፡፡ ጠንክሮ መጸለይ ነው” አለኝ በትሕትና፡፡

“እሺ ወንድሜ፡፡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ የመጣሁት ከእመቤታችን በረከት ለማግኘት ነው፤ ለዚህም እግዚአብሔር ይረዳኛል፡፡” በማለት አመስግኜ ተሰናበትኩት፡፡ “ብዙ ኃጢአት ባለችበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች” የሚለው የቅዱስ ኤፍሬም የሰኞ ውዳሴ ማርያም ጸሎት ትዝ ብሎኝ እየተገረምኩ አንድ ጥግ ድንጋይ ላይ ተቀመጥኩ፡፡

ሰርክ ላይ ጸሎት፣ የወንጌል ትምህርት እንዲሁም ምሕላ ተደረገ፡፡ ሱባዔው ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ ምእመናን ሥነ ምግባር በተሞላበት ሁኔታ የመጡበትን ዓላማ አሳክተው እንዲመለሱ፣ የበረከቱ ተሳታፊም እንዲሆኑ በመምህራን ማሳሰቢያ ተሰጠ፡፡

የሰዓታት ጸሎት መርሐ ግብር እስኪጀመር ድረስ ሁሉም ወደየበአቱ በማምራት በሶውን በጥብጦ፣ ቆሎውን፣ ሽምብራውን ቆርጥሞ የበረታ በጸሎት ሲጠመድ ሌላው ዕረፍት አደረገ፡፡ አንዳንዶች ከአሁኑ አርምሞ ጀምረዋል፡፡ አዳራሹ ውስጥ በቡድን ሆነው የመጡት ጓደኛማቾች ድምጻቸውን ይቀንሱ እንጂ መቀላለዳቸውን አላቋረጡም፡፡ በጸሎት ለተጠመደ ኅሊናን ይሰርቃሉ፡፡

ከሌሊቱ ዐራት ሰዓት ሲሆን የቤተ ክርስቲያኑ ደወል ተደወለ፡፡ አንዱ አንዱን እየቀሰቀሰ ተያይዘን ወደ ቤተ መቅደሱ አመራን፡፡ ካህናት አባቶች ሰዓታት ቆመዋል፡፡

ቤተ መቅደሱ የቻለውን ያህል ምእመናንን አስተናግዶ ሌላው ውጪ ሆኖ ብርዱን ተቋቁሞ ይጸልያል፡፡ ሰዓታት እንደ ተጠናቀቀ ንጋት ላይ የኪዳን ጸሎት፣ ስብሐተ ነግህ ቀጠሉ፡፡ ጨለማው ለብርሃን ሥፍራውን ሲለቅ ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ እንደ ቅደም ተከተላቸው ቀርበው የቅዳሴ ሰዓት እስኪደርስ ጸበል ለመጠመቅ እሽቅድድም በሚመስል ፍጥነት ይራወጣሉ፡፡

ጸበል መያዣ ባለ አምስት ሊትር ጀሪካን ይዤ ወደ ጸበሉ ስፍራ ሰዎችን ተከትዬ ሔድኩ፡፡ ግርግሩ ዕረፍት ይነሣል፡፡ እንደማንኛውም ሰው ወረፋ ያዝኩ ነገር ግን በጉልበታቸው የተመኩ ወጣቶች እየተጋፉ፣ የዕድሜ ባለጠጋ የሆኑትን አረጋውያንን እየገፉ ተጠምቀው ለመውጣት ይጣደፋሉ፡፡ ሰልፉ ተረበሸ፡፡ ችግሩ ከሚያስተናግዱ ወንድሞች በላይ ሆነ፡፡ በሴቶችም በኩል መጠነኛ ግርግሩ ቀጥሏል፡፡ በዚህ መካከል የሚወድቅ፣ ንብረቱ የሚዘረፍ ቁጥሩ በርካታ ነው፡፡ የምእመናን ቁጥር ከፍተኛ ቢሆንም እስከ ስድስት ሰዓት ሳይጠመቅ የተመለሰ አልነበረም፡፡

ከቅዳሴ በኋላ ዕረፍት የሚያደርጉ እንዳሉ ሁሉ ተፈትተው የተለቀቁ ይመስል ከበአታቸው እየወጡ በቡድን፣ በቡድን እየሆኑ በየጫካው ለፌዝና ለቀልድ ጊዜያቸውን የሰጡ ምእመናንም አሉ፡፡ ነገር ግን የመጡት ለሱባዔ ነው፡፡

እንዲህ እንዲህ እያልን ነሐሴ ፲፮ ቀን ድረስ ቆየን፡፡ የእመቤታችን ትንሣኤ ተበሠረ፡፡ ከቅዳሴ በኋላ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ ያክብሩት ብላ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት እንደ ሠራች በስፋት አስተማሩ፡፡ የሱባዔውንም መጠናቀቅ አወጁ፡፡

ቤተ ክርስቲያኗ ከጥሉላት ምግቦች ተከልክሎ የቆየውን ምእመን የጾም መፍቻ ብላ ያዘጋጀችው ማዕድ በየአዳራሹና በድንኳኑ ታደለ፡፡ እኔ ካለሁበት አዳራሽ ውስጥ ካሉት ምእመናን መካከል “አንበላም እስከ ነሐሴ ፳፩ ቀን ጾማችንን እንቀጥላለን” በማለት የመለሱት ይበዛሉ፡፡ ግራ ተጋባሁ፡፡ የቀረበላቸውን ተቃምሰው ጓዛችን ሸክፈው ወደወጡበት ቤታቸው ለመመለስ የሚጣደፉ ምእመናንም ቁጥር ብዙ ነው፡፡ እኔ ግን አንድ ቀን እረፍት አድርጌ በማግስቱ ለመሔድ ስለወሰንኩ የቀረበልኝን ማዕድ በላሁ፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በመጣሱ ቅር ተሰኘሁ፡፡ ቤተ ክርስቲያን “የእመቤታችንን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ አክብሩ” እያለች ይህንን ተላልፈው የእመቤታችን ትንሣኤ በሚከበርበት ወቅት እጾማለሁ ማለት ምን ማለት እንደሆነ አልገባኝም፡፡ “ቤተ ክርስቲያን ሁለት ዓይነት ሥርዓት አላት እንዴ?” እያልኩ ከራሴ ጋር ሙግት ገጠምኩ፡፡ አንድ ነገር ወሰንኩ፡፡ አባቶችን ማማከር፡፡

ጥቂት ዕረፍት አድርጌ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር በመግባት አባቶችን ፈለግሁ፡፡ ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜን ላለፉት ቀናት በጣፋጭ አንደበታቸው ሲተረጉሙ የነበሩት አባት ከቤተ መቅደስ ሲወጡ አገኘኋቸው፡፡ ቀረብ ብዬ ሰላምታ ከሰጠኋቸው በኋላ ጥያቄዬን አቀረብኩ፡፡

በትኩረት እየቃኙኝ “ልጄ ቤተ ክርስቲያን የሠራችው ሥርዓት ማፋለስ ኃጢአት ነው፡፡ እውነት ነው ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ ያክብሩት ብላ ሠርታለች፡፡ ነገር ግን ምእመናን ሲጥሱት እንመለከታለን፡፡ ከዚህ በፊትም በስፋት አስተምረናል፡፡ የበለጠ በረከት ለማግኘት ነው” እያሉ የሚጾሙ ምእመናን ቁጥር በርካታ ነው፡፡ ይህ ትክክል አይደለም፡፡ አንዳንድ ምእመናን ቢነገራቸውም አይሰሙም፡፡ ግዝት አይደለም መጾም እንችላለን ይሉሃል፡፡ አንዳንድ አባቶችንም ስታነጋግር ምን ችግር አለው ይሉሃል፡፡ ነሐሴ ፳፩ ቀንም ታቦት አውጥተው ያከብራሉ፡፡ ይህ ትክክል አይደለም፡፡” አሉኝ ጥያቄው የእኔ ብቻ ሳይሆን የእሳቸውም ጥያቄ እንደሆነ በሚገልጽ ምላሽ፡፡

“ታዲያ ሥርዓት የሚሽሩትን ከገዳሙ ለምን አታስወጡም” አልኳቸው፡፡

ለጥቂት ሰከንዶች በመገረም እያዩኝ፡፡ “ልጄ እኔ የዚህ ሥልጣን የለኝም፡፡ በተቻለኝ አቅም ልጆቼን በሔዱበት ሁሉ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት እንዳይጥሱ አስተምሬአቸዋለሁ፡፡ ካለ እኔ ፈቃድም አያደርጉትም፡፡ አሁን አንተ የምትለኝን ገዳሙ የራሱ አስተዳደር አለውና እነሱን ጠይቅ” ብለው መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ አስተዳደሩን ለማግኘት ያደረግሁት ጥረት ሳይሳከ ቀረ፡፡

ሁላችንም ምክንያት የምናደርገው ሌሎችን ነው፡፡ ለምን ብለን ግን አንጠይቅም፡፡ ፈቃጁ ማነው? ማን እንደሆነ አይታወቅም፡፡ አንዱ ወደ አንዱ ያሻግርሃል፡፡ በጣም ተበሳጨሁ፡፡ ወደ አዳራሹ ተመለስኩ፡፡ ብዙ ሰዎች ሱባኤያቸውን ቀጥለዋል፡፡ በመብላቴ እኔን እንደ ደካማና ኃጢአተኛ አድረገው የቆጠሩኝ መሰለኝ፡፡ ሕሊናዬ አላርፍ አለኝ፡፡

አዳራሹ ውስጥ ካሉት መካከል ለረጅም ሰዓት ቆሞ በመጸለይና በመስገድ መንፈሳዊ ቅናት ወደ ቀናሁበት ወንድም ጠጋ ብዬ ጥያቄዬን አቀረብኩለት፡፡ “ጾሙ አልተጠናቀቀም ወይ?” ነበር ጥያቄዬ፡፡

“በረከት ለማግኘት ስል እስከ እመቤታችን ዕረፍት መታሰቢያ ቀን ድረስ እቆያለሁ፡፡” አለኝ፡፡

“ለምን? ሥርዓት መጣስ አይሆንብህም?” አልኩት፡፡

“መብቴ እኮ ነው፡፡ ከመብላት አለመብላት ይሻላል፡፡” አለኝ፡፡

“እንዴት እንዴት አድርገህ ነው የምትተረጉመው? ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን ትንሣኤ ከነሐሴ ፲፮-፳፩ ቀን እንደ በዓለ ሃምሳ ያክብሩት በማለት መደንገጓን ምነው ዘነጋህ? ለመሆኑ ሱባኤው እስከ ነሐሴ ፳፩ ቀን መቆየት የተጀመረው መቼ ነው?” አልኩት፡፡

“በቅርብ ይመስለኛል፡፡ ግን ምን ችግር አለው? ቀኖና ነው፡፡ ቀኖና ደግሞ ይሻራል፣ ይስተካከላል፡፡ አባታችን ይህንን ሲናገሩ ሰምቻለሁ” አለ በድፍረት፡፡

“ማናቸው አባትህ?” አልኩት ዐይን ዐይኑን እየተመለከትኩ፡፡

“ባሕታዊ እከሌ ናቸዋ” አለኝ፡፡

በጣም አዘንኩ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተዘንግቶ፣ ቀድሞ አባቶች የሠሩትን ሥርዓት በባህታዊ ነኝ ባዮች ሲሻር ያሳዝናል፡፡

“ለመሆኑ ማነው የሚሽረውና፣ የሚያስተካክለው?” አልኩት እልህ እየተናነቀኝ፡፡

“ቤተ ክርስቲያን ናታ፡፡”

“የቤተ ክርስቲያን መብት ከሆነ አንድ ባሕታዊ ይህንን የመሻር ምን ሥልጣን አለው? ለምእመኖችዋ ውሳኔውን ማሳወቅ ያለባት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ እሷ ደግሞ አባቶች የሠሩትን ሥርዓት የምታጸና እንጂ የምታፈርስ አደለችም፡፡” አልኩት በንዴት፡፡

“አንተ እንደፈለግህ፡፡ እኔ ግን የባሕታዊ አባቴን ድምጽ እሰማለሁ፡፡ በቃ አትጨቅጭቀኝ፡፡” በማለት በኩርፊያ ጥሎኝ ሄደ፡፡

ለመሆኑ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሲጣስ አደብ የሚያስገዛው ማነው? ለማንስ አቤት እንበል? ሱባኤያችን በረከት የሚያሰጥ ይሆን ዘንድ ምን እናድርግ? ሱባኤ ሔጄ ይህንን ታዘብኩ፡፡ እናንተስ ምን ትላላችሁ?

በዓለ ደብረ ታቦር

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት በወርሐ ነሐሴ ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ የደብረ ታቦር በዓል ነው፡፡ ይህንንም አስመልከቶ ቅዱስ ወንጌል ሲነግረን፡- ጌታችን ኢየሱስም ወደ ፊልጶስ ቂሣሪያ ሀገር በደረሰ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን “የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?” ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም “መጥምቁ ዮሐንስ ነው የሚሉ አሉ፣ ሌሎችም ኤልያስ፣ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ” አሉት፡፡ እርሱም “እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” አለው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ደቀ መዝሙሩን ቅዱስ ጴጥሮስን   “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ ብፁዕ ነህ፤ በሰማይ ያለው አባቴ ነው እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህም፡፡” በማለት መለሰለት፡፡ (ማቴ. ፲፮÷፲፫-፳፤ ፲፯፥፩-፰)

ይህም በሆነ በስድስተኛው ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን ደቀ መዛሙርት ማለትም፡- ቅዱስ ጴጥሮስን፣ ቅዱስ ዮሐንስንና ቅዱስ ያዕቆብን ይዞ ሌሎቹን ደቀ መዛሙርት ደግሞ በእግረ ደብር (በተራራው ሥር) ትቶ ወደ ታቦር ተራራ ወጣ፡፡ በዚያም ሙሴን ከመቃብር፣ ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን ጠርቶ በፊታቸው ብርሃነ መለኮቱን ገለጠላቸው፡፡ ይህ ጌታችን መድኃኒታችን ብርሃነ መለኮቱን ክብረ መንግሥቱን የገለጠበት ዕለትም በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከሚከበሩ ዐበይት በዓላት ውስጥ አንዱ ሆኖ በየዓመቱ ከነሐሴ ፲፫ ቀን በድምቀት ይከበራል፡፡ ከዋዜማው ነሐሴ ፲፪ ቀን ጀምሮ በሊቃውንቱ የሚቀርበው ስብሐተ እግዚብሔር ዕለቱን የሚያዘክር ነው፡፡

በዓሉ በምእመናን ዘንድ “ቡሄ” በመባል ይታወቃል፡፡ በሀገራችን ኢትዮጵያም ክረምቱ፣ ጭጋጉ፣ ደመናው ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታይበት ጊዜ በዚሁ በዓል አካባቢ ስለሆነ በዓሉ የ“ቡሄ” በዓል ተብሎ ይጠራል፡፡ በዓለ ደብረ ታቦር ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት፤ ብርሃን የታየበትና ድምፀ መለኮቱ የተሰማበም ዕለት በመሆኑም “የብርሃን” በዓል ይባላል፡፡

የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ብርሃን፣ ወገግታ የሚታይበት፤ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚሸጋገርበት ወቅት በመሆኑ ከደብረ ታቦር በዓል በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ “ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት” እንዲሉ ኢትዮጵያውያን በብሂላቸው፡፡

ከላይ በጥቂቱ ለመግለጽ እንደሞከርነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን ደቀ መዛሙርት ወደ ተራራው ይዟቸው ከወጣ በኋላ “መልኩም በፊታቸው ተለወጠ፤ ፊቱም እንደ ፀሐይ አበራ፤ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ሆነ፡፡ እነሆ ሙሴ እና ኤልያስም ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው፡፡” በማለት ብርሃነ መለኮቱን መግለጡን መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳናል፡፡ (ማቴ. ፲፯፥፪-፫) በዚህ ወቅት ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፡፡ ከደመናው ውስጥም “የምወደው፤ በእርሱም ደስ የሚለኝ ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” የሚል ቃል መጣ፡፡ ይህም የቅድስት ሥላሴን አንድነትና ሦስትነት በታቦር ተራራ ላይ መገለጹን ያመለክተናል፡፡

ለምን ወደ ተራራ ይዟቸው ወጣ?

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ወደ ተራራ ይዟቸው የወጣው ስለ ሁለት ነገር እንደሆነ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስተምራሉ፡፡ የመጀመሪያው፡- በማርቆስ ወንጌል ላይ የእግዚአብሔር መንግሥት እስክትመጣ ድረስ ሞትን የማይቀምሱ እንዳሉ አስተምሯቸው ነበርና ይህ እውነት መሆኑን ለማሳየት ወደ ተራራ ይዟቸው ወጥቷል፡፡ “እውነት እላችኋለሁ በዚህ ከቆሙት ሰዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት በኃይል ስትመጣ እስኪያይዋት ድረስ ሞትን የማይቀምሱት አሉ” እንዲል ኤልያስን ከብሔረ ሕያዋን አምጥቶ አሳይቷቸዋል፡፡ (ማር. ፱፥፩) ሁለተኛው፡-  በዚህ ዕለት ምሥጢረ ሥላሴን እንዲረዱ የሦስትነት ምሥጢር ገልጦ ያሳያቸው ዘንድ ወደ ተራራ ይዟቸው ወጥቷል፡፡ ሌላው “ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ ወይሴብሑ ለስምከ፤ ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፤ ስምህንም ያመሰግናሉ” ሲል ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በትንቢት ተናግሮ ነበርና ይህ ይፈጸም ዘንድ ወደ ተራራ ይዟቸው ወጥቷል፡፡ (መዝ. ፹፰፥፲፪-፲፫)

ዘጠኙን ሐዋርያት ከተራራው ግርጌ ለምን ተዋቸው? 

ዘጠኙን ደቀ መዛሙርት ከታቦር ተራራ ግርጌ ትቷቸው ሦስቱን ብቻ ይዟቸው ወጥቷል፡፡ ለምን ቢሉ፡- ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳልም ሄዶ ከሽማግለዎች፣ ከካህናትና ከጻፎች ብዙ መከራ እንደሚቀበል፣ እንደሚሞትና በሦስተኛውም ቀን እንደሚነሣ ለደቀ መዛሙርቱ ሲነግራቸው ቅዱስ ጴጥሮስ ግን ለጌታው ካለው ጽኑ ፍቅር፣ እንደዚሁም  በዚህ ምድር ላይ ሳለ ሹመት ሽልማትን ይሻ ነበርና “አቤቱ ይህ አይሁንብህ፤ ከቶም አይድረስብህ” አለው፡፡ (ማቴ.፲፮፥፳፪)፤ እንዲሁም ሁለቱ ደቀ መዛሙርት ዮሐንስና  ማርቆስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን ዓለም ለመግዛት የመጣ ስለመሰላቸው እናታቸው “እነዚህን ሁለቱ ልጆቼ በመንግሥትህ አንዱን በቀኝህ፣ አንዱን በግራህ እንዲቀመጡ አድርግልኝ” ብላ በተማጸነች ጊዜ ጌታችን “የምትለምኑትን አታውቁም፤ እኔ የምጠጣውን ጽዋ መጠጣት ትችላላችሁን? እኔስ የምጠመቀውን ጥምቀት ትጠመቃላችሁን?” አላቸው፡፡ እነርሱም “አዎን እንችላለን” ብለው መልሰዋል፡፡ (ማቴ. ፳፥፳-፳፫)

ይህም ልክ እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ምድራዊ ሹመትን መሻታቸው፣ እንዲሁም ለጌታቸው ጽኑ ፍቅር እንዳላቸው ለመግለጽ ይህንን ብለዋልና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምድራዊ አምላክ ብቻ ሳይሆን ይህን ዓለም ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣ መሆኑን፣ በኋላም ይህን ዓለም እንደሚያሳልፋት፣ ምድራዊ ብቻ ሳይሆን ሰማያዊ አምላክ መሆኑን ለማሳየት ሦስቱን ወደ ተራራው ይዟቸው ወጥቷል፡፡ በዚያም ብርሃነ መለኮቱን ገለጠላቸው፡፡ ለሦስቱ የገለጠላቸውን ምሥጢርም ምንም የሚሳነው ነገር የሌለው አምላክ ነውና በእግረ ደብር ላሉት ለስምንቱ ሐዋርያትም ገልጦላቸዋል፡፡ ምነው ይሁዳን ተወው ስንል ደግሞ ይሁዳ አሳልፎ እንደሚሰጠው ያውቃልና ይህንን ምሥጢር ያይ ዘንድ ስላልፈቀደ ነው፡፡ ስለዚህም ይሁዳን ለመለየት ዘጠኙን ከተራራው ግርጌ አቆይቷቸዋል፡፡

ጅራፍ፡-

የደብረ ታቦር በዓል ከመድረሱ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ በገጠሪቱ የሀገራችን ክፍሎች ልጆች ባለ ሦስት ግምድ ጅራፍ ገምደው ከብቶች እየጠበቁ ማጮህ ይጀምራሉ፡፡ ይህም በዕለቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ጊዜ አብ በደመና ሆኖ “የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት” ሲል የተናገረው ድምጽ ምሳሌ ነው፡፡ ከድምጹ አስፈሪነት የተነሣም ሦስቱም ሐዋርያት በግምባራቸው ወደ መሬት መውደቃቸውን ቅዱስ መጽሐፍ ያስረዳናል፡፡ “ደቀ መዛሙርቱም ሰምተው በግምባራቸው ወደቁ” እንዲል፡፡ (ማቴ. ፲፯፥፮) 

ሙልሙል ዳቦ፡-

የሙልሙል ዳቦ ትውፊታዊ አመጣጥ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዕለት ደብረ ታቦርንና ዙሪያውን በብርሃን መልቶት ስለነበር በዚያ የነበሩ ሕፃናት እረኞች ቀኑ የመሸ ስላልመሰላቸውም ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ በዚያው ሆነው ከብቶቻቸውንና በጎቻቸውን እየጠበቁ ቆይተዋል፡፡ ይህ የልጆቻቸው ያለ ወትሮው መዘግየት ያሳሰባቸው ወላጆቻቸውም በፍጥነት የሚደርሰውን ያልቦካ ዳቦ ጋግረው ይዘውላቸው የመሄዳቸው ምሳሌ ነው፡፡

በዚህም ምክንያት ኦርቶዶክሳውያን ሙልሙል ዳቦ ጋግረው ልጆች ዕለቱን በማሰብ “ቡሄ በሉ” እያሉ በየቤታቸው ሲመጡ ሙልሙል ዳቦ ይሰጣቸዋል፡፡ ሕፃናቱም የጌታን በዓል ሊያበሥሩ እየዘመሩ ሲመጡ የምሥራች (ወንጌልን) ይዘው ወደ ምእመናን የተላኩት የደቀ መዛሙርት ምሳሌ ናቸው፡፡ ምእመናን ድምጻቸውን ሰምተው ለሕፃናቱ መስጠታቸውም ምእመናን የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት በክብር የመቀበላቸውንና በእነርሱ የተሰበከላቸውነ የክርስቶስን ቃል የመስማታቸው ምሳሌ ነው፡፡ ሐዋርያት በገቡበት ሀገር ሁሉ አስተምረው አጥምቀው የጸጋ ልጅነትን አሰጥተው እንደሚቆዩ ሁሉ ልጆችም ዘምረው አመስግነው መርቀው “ውለዱ ክበዱ የመንግሥተ ሰማያት ወራሾች ያድርጋችሁ” ብለው አመስገነው ይሄዳሉና ሕፃናቱ በሐዋርያት ይመሰላሉ፡፡

ችቦ

ችቦ የጌታችንን ብርሃነ መለኮት መገለጥ የሚያመለክት ነው፡፡ በመሆኑም ችቦ ለኩሰን በዓሉን እናከብራለን፡፡ የዚህ ችቦ ትውፊታዊ አመጣጥም በብርሃኑ ድምቀት የቀኑን መምሸት ያልተረዱ እረኞች በሜዳ መቅረታቸው ምክንያት ወላጆች ከየመንደራቸው ችቦ ለኩሰው ልጆቻቸውን ፍለጋ የሄዱበትን ታሪክ እያዘከርን በዓሉን እናከብራለን፡፡

በአጠቃላይ በታቦር ተራራ ላይ፡-

  • “ታቦርና አርሞንኤም በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል” (መዝ. ፹፰፥፲፪) ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመ።
  • መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም አምላክነቱን ገለጠ።
  • ምሥጢረ ሥላሴ ተገለጠ/አብ በደመና ድምጹን በማሰማት፣ መንፈስ ቅዱስ በብርሃን፣ ወልድ በአካል/።
  • ሙሴ፦ “እኔ ጠላት ብገድልም፣ ደመና ብጋርድም፣ መና ባወርድም፣ እስራኤልን ከክፋታቸው መልሶ ማዳን አልተቻለኝም። ለአንተ ግን ሁሉ ይቻልሃል። ደግሞስ የእኔን ፈጣሪና ጌታ እንዴት ሙሴ ይሉሃል? የሙሴ ጌታ ይበሉህ እንጂ” በማለት የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት መሰከረ።
  • ኤልያስ፦ “እኔ ሰማይ ብለጉም፣ እሳት ባዘንብም እስራኤልን ከክፋታቸው መልሶ ማዳን አልተቻለኝም። ለአንተ ግን ይቻልሃል። ደግሞስ የኔን ፈጣሪና ጌታ እንዴት ኤልያስ ይሉሃል? የኤልያስ ጌታ ይበሉህ እንጂ” በማለት የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት መሰከረ።
  • ቅዱስ ጴጥሮስም በሕይወት፣ በእምነት፣ በቤተ ክርስቲያንና በአገልግሎት መኖር መልካም እንደሆነ ሲገልጥ “በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው” በማለት ተናገረ።
  • የእግዚአብሔር መንግሥት ሕጉን ጠብቀው ለሚኖሩ ለሁሉም መሆኑን ለማጠየቅ ሙሴን ከአገቡት፣ ኤልያስን ከደናግልና ሐዋርያትን ከዓለም አምጥቶ አሳየን።
  • ደብረ ታቦር የወንጌል፣ የመንግሥተ ሰማያት የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ መሆኗን፤ ነቢያት በትንቢትና በምሳሌ፣ ሐዋርያት በግልጥና በተግባር የሰበኳት መሆኗን ገለጠ።

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በነቢያትና በሐዋርያት መሠረትነት ላይ የጸናች (በነቢያት ትንቢት፣ በሐዋርያትም ስብከት ላይ ሳትናወጽ ጸንታ የቆመች) መሆኗን ለማጠየቅ የብሉይ ኪዳን ነቢያትንና የሐዲስ ኪዳን ሐዋርያትን ወደ ተራራው ጠርቶ ብርሃነ መለኮቱን ገለጠላቸው፡፡

ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን። አሜን!

ሕይወት ከግቢ ጉባኤ በኋላ

በእንዳለ ደምስስ

ማኅበረ ቅዱሳን ላለፉት ሠላሳ ዓመታት በመላው ዓለም በሚገኙ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የግቢ ጉባኤያትን በመመሥረት ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ዶግማ እና ቀኖና እንዲሁም ሥርዓት እንዲያውቁ፣ ራሳቸውንም ከከፉ በመጠበቅ መንፈሳዊ ሕይወታቸውን ማነጽ እንዲችሉ አገልገሎቱን በማጠናከር ከፍተኛ ሥራ ሲሠራ ቆይቷል፡፡

በእነዚህም ዘመናት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎችን አስተምሮ በአባቶች ቡራኬ ማስመረቅ የቻለ ሲሆን፤ ተመርቀው ሲወጡም በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ጠንክረው በሚሄዱበት ሁሉ በተሰማሩበት የሥራ መስክ ሀገራቸውን፣ እንዲሁም በተማሩት የቤተ ክርስቲያን ትምህርት እንደ ጸጋቸው መልሰው ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ መመሪያ ይሰጣቸዋል፡፡ በተጣለባቸው ኃላፊነት መሠረት በርካቶች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚገኙ መዋቅሮች ማለትም በማኅበረ ቅዱሳን ማእከላትና ወረዳ ማእከላት፣ በሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ በሰበካ ጉባኤያት፣ በተለያዩ የጉዞና የጽዋ ማኅበራት በመሳተፍ አገልግሎት ሲሰጡ ማየት የተለመደ ነው፡፡

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ በነበሩበት ወቅት ራሳቸውን ከኃጢአት ሥራና አልባሌ ሥፍራ በማራቅ በትምህርታቸው ውጤታማ ሆነው ሜዳልያና ዋንጫ በመሸለም ለሌሎች ምሳሌ በመሆንም ይታወቃሉ፡፡ ከመደበኛ ትምህርታቸው በተጨማሪም ማኅበረ ቅዱሳን የሚሰጠውን ተከታታይ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከመማር አልፈው የአብነት ትምህርትን በመከታተል ዲያቆን፣ መሪጌታ እየሆኑ መውጣትም እንደሚቻል በተግባር ያሳዩ በርካቶች ናቸው፡፡

በግቢ ጉባኤ ቆይታቸው ከትምህርታቸው በተጨማሪ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውም ለማደግ የሚያደርጉት ጥረት ከፍተኛ በመሆኑ ሲወጡም ቤተ ክርስቲያንና ሀገራቸውን በማገልግል ላይ የሚገኙ በሄዱበት ሁሉ በአገልግሎት በማሳተፍ በልዩ ልዩ ሙያዊ ዘርፎች ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዕድገት ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት ያበረክታሉ፡፡

በተቃራኒው ደግሞ በግቢ ጉባኤ ውስጥ እያሉ በአገልግሎትም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዳልበረቱ ሁሉ ትምህርታቸውን አጠናቀው ሲወጡ ግን ያንን ጥንካሬአቸውን ይዘው መቀጠል ይቸገራሉ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “በዓለም ግን መከራ ትቀበላላችሁ፤ ነገር ግን ጽኑ፤  እኔ ዓለምን ድል ነስቼዋለሁና” ብሎ እንዳስተማረው በጽናት ዲያብሎስ ያዘጋጀውን ወጥመድ ሁሉ ሰባብሮ ከማለፍ ይልቅ በቀላሉ ዓለም ባዘጋጀላቸው ወጥመድ ውስጥ ይወድቃሉ፡፡ (ዮሐ.፲፮፥፴፫)፡፡

ነገር ግን ለተጠሩበት ዓላማ መታመን ከእያንዳንዳቸው ይጠበቃልና ለሚገጥሟቸው ፈተናዎች ሁሉ ከመንበርከክ በጽናት ማለፍ ይገባል፡፡ በተለያዩ ሰንካላ ምክንያቶችም በማመካኘት ከአገልግሎትና ከመንፈሳዊነት መራቅ አያድናቸውምና፡፡

ከምረቃ በኋላ የሚያጋጥሟቸውን የሕይወት ጉዞዎች በመንፈሳዊ ሕይወት መመዘን፡-

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ ወደ ማኅበረሰቡ የመቀላቀል ዕድል ስለሚያገኙ በትምህርት ላይ ካሳለፉት ሕይወት በተለየ መልኩ ዓለም በሯን ከፍታ ትቀበላቸዋለች፡፡ ራሳቸውን ችለው የሚቆሙበት ጊዜ ደርሷልና በበርካታ ጉዳዮች የመሳተፍ ዕድል ይገጥማቸዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፡-

  • ሥራ
  • አገልግሎት
  • ማኅበራዊ ሕይወት
  • ጋብቻ

ከላይ ከተጠቀሱት በተጨማሪ ሌሎችም ጉዳዮች ቢኖሩም እነዚህን አንድ በአንድ እንመለከታቸዋለን፡፡

፩. ሥራ፡-

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ገና ከከፍተኛ ትምህርት ተቋም እንደወጡ ሥራ ማግኘት ትልቁና ከባዱ ፈተና ነው፡፡ ነገር ግን ብዙ ውጣ ውረድ ቢኖረውም ይህንን ተቋቁመው ሥራ የማግኘት ዕድል ይገጥማቸዋል፡፡ ከሥራ ጋር ተያይዞ ደግሞ የሥራውን ባሕርይ፣ የመሥሪያ ቤቱን ባህል ለመልመድ ጥረት ያደርጋሉ፤ ይህን ሲያደርጉ በተለይም ከአገልግሎት፣ ከጸሎት፣ በአጠቃላይ ከመንፈሳዊ ሕይወት የመዘናጋት ሁኔታ ሊያጋጥማቸው ይችላል፡፡ ነገር ግን በግቢ ጉባኤ ውስጥ እያሉ ያገኙት ዕውቀት፣ የቀሰሙት ልምድ፣ እንዲሁም የጸሎት ሕይወት ስለሚናፍቃቸው ከሥራቸው በተጨማሪ እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ ለመጓዝ አይቸገሩም፡፡

ሥራ ለማንኛውም የሰው ልጅ መሠረታዊ ጉዳይ ስለሆነ ራስን በራስ የማስተዳደር፣ ቤተሰብን የመርዳት ዓላማ ተግባራዊ የሚያደርጉበት ወቅት ስለሆነ ይበልጥ ኃላፊነት እንዲሰማቸው ያደርጋቸዋል፡፡ ሥራ መያዛቸው በርካታ ጥያቄዎችን የሚፈታላቸው በመሆኑ ቀስ በቀስ ወደ አቋረጡት አገልግሎት በመመለስ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን መዋቅር ማለትም በማኅበረ ቅዱሳን፣ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ፣ በአገልልገሎትና በጽዋ ማኅበራት ውስጥ ሲሳተፉ መመልከትም የተለመደ ነው፡፡ በተለይም ለአገልግሎት የሚያበቃቸውን ሥልጠና ማኅበረ ቅዱሳን ባሉት መዋቅሮቹ አማካይነት በመስጠት መምህራን በሌሉባቸው ቦታዎች በመሸፈን፣ ክህነትም ካላቸው በጎደለው ቦታ ሁሉ ገብተው ያገልግላሉ፡፡ ይህም ባይቻል ግን ራሳቸውን አርአያ ያለው ክርስቲያን ይሆኑ ዘንድ በማብቃት መልካም ቤተሰብን ያፈራሉ፡፡

አንዳንዶቹም ገና ከከፍተኛ ትምህርት ተመርቀው ሲወጡ ወደ ቤተሰቦቻቸው ሲመለሱ ወደ አገልግሎት መመለስ እንኳን ባይችሉ በአጥቢያቸው በሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ኪዳን የማድረስ፣ ቅዳሴ የማስቀደስ፣ ራሳቸውንም ከመንፈሳዊ ሕይወት ጋር ማቆራኘቱ ላይ ይተጋሉ፡፡ ሥራ ቢያገኙም ባያገኙም በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ዙሪያ የሚመጣባቸውን ፈተና ሁሉ ይጋፈጣሉ፡፡ የንስሓ አባት የመያዝ፣ የምሥጢራት ተካፋይ የመሆን፣ በጸሎት የመበርታት ዕድላቸውም ከፍተኛ ነው፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ከሥራ ማግኘት ጋር ከሚያጋጥሟቸው ፈተናዎች መካከል ዋነኛው የኢኮኖሚ ጉዳይ ከሞላ ጎደል በመመለሱ ለሌሎች ፍላጎቶች የመጋለጥ ዕድላቸውም ከፍተኛ መሆን ነው፡፡ መንፈሳዊ ፍሬን ከማፍራት ይልቅ አንቱ አንቱ እንዲባሉ ይተጋሉ፡፡ መንፈሳዊነትን እርግፍ አድርገው በመተዋቸውም የበላቸው ጅብ አልጮህ ይላል፤ ጠፍተውም ይቀራሉ፡፡ ይህ ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚፈልግ ጉዳይ በመሆኑ በመንፈሳዊ ሕይወት አልፈዋልና መፍትሔውን ሁሉ ከእግዚአብሔር ጋር በመነጋገር በሰከነ መንፈስ ማየትና መፍታትን ይጠይቃል፡፡

ግባቸው ሥራ ማግኘት ላይ ብቻ ገድበው ዓላማቸው ሲሳካ የመጡበትንና ያለፉበትን ሕይወት በመርሳት ለአልባሌ ነገር ይጋለጣሉ፡፡ በተለይም ገንዘብ ማግኘታቸው ሁሉን ማድረግ እንደሚችሉ አድርጎ ዲያብሎስ ስለሚያተጋቸው ይህንን ተቋቁመው ማለፍ ባለመቻላቸው ወድቀውና ባክነው ይቀራሉ፡፡ ለቤተሰብ ያለመታዘዝ፣ ክፉንና ደጉን አለመለየት፣ ሁሉንም ነገር ሞክሬ ካላየሁ የሚል ስሜት ውስጥ በመግባት ሕይወታቸውን ያበላሻሉ፡፡ አንድ ጊዜ ከገቡ መውጣት ስለሚቸገሩም ከቤተ ክርስቲያንም ከአገልግሎትም ይርቃሉ፤ መንፈሳዊነታቸውንም እርግፍ አድርገው ይጥላሉ፡፡

እነዚህ ከላይ ያየናቸው ሁለት ገጽታዎች ጎልተው የሚታዩ ሲሆን ይህንን ችግር ለመፍታት ቤተሰብ ትልቁን ድርሻ ቢወስድም እንደ ተቋም ማኅበረ ቅዱሳን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሰጠችው ኃላፊነት መሠረት በግቢ ጉባኤ ውስጥ አልፈው የተመረቁ ተማሪዎችን ባለው መዋቅር የመከታተል ግዴት አለበት፡፡ በተለይም ከማእከላትና ወረዳ ማእከላት ብዙ ይጠበቃል፡፡

፪. አገልግሎት፡-

አገልግሎት በአንድ ወቅት ብቻ በሕይወት ተተግብሮ የሚጠናቀቅ ጉዳይ አይደለም፡፡ የአባቶቻችንም ሕይወት እንዲሚያስተምረን እስከ ሕይወት ፍጻሜአቸው ድረስ የሚገጥማቸውን ፈተና ሁሉ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ  ማለፋቸውን ነው፤ ቅዱሳት መጻሕፍትም የሚያስተምሩን ይህንኑ ነው፡፡  “እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል” እንዲል፡፡(ማቴ. ፳፬፥፲፫)

አገልግሎት ከራስ ይጀምራል፤ ራስን በመንፈሳዊ ሕይወት በማነጽ ለሌሎች ብርሃን መሆንን የሚጠይቅ ነው፡፡ ራስን በመንፈሳዊ ሕይወት ከማነጽ ጀምሮ ቤተሰብን፣ ጎረቤትን፣ ማኅበረሰብን፣ ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል ከአንድ መንፈሳዊ ሰው የሚጠበቅ መሠረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት ባደግን ቁጥር ለአገልግሎት መፋጠናችንም እያደገ ይመጣል፡፡  ከዚህ አንጻር ከግቢ ጉባኤያት ተመርቀው ሲወጡ በሄዱበት ሁሉ ለአገልግሎት ራሳቸውን ማዘጋጀት፣ ከዚህ,ያም አልፎ በጎደለው በኩል በመቆም ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡ በተለይም ቤተ ክርስቲያን ብዙ ትጠብቅባቸዋለች፡፡

አንዳንዶች ግን በግቢ ጉባኤያት በቂ ዕውቀትን በመቅሰም የጀመሩትን የክርስትና ሕይወት ከምረቃ በኋላ ወደ ቤተሰቦቻቸው ሲመለሱ ሥራ እስኪያገኙ ድረስ አገልግሎት ላይ ሲዘናጉ እንመለከታቸዋለን፡፡ ያለ መሰልቸት በሥራ አስፈጻሚነትና በተለያዩ የአገልግሎት ክፍሎች እንደ ፀጋቸው ሲያገለግሉ እንዳልነበር ከዚያ ሲወጡ ግን ዕረፍት እንደመውሰድ ወደ ኋላ የሚሉ እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ብዙውን ጊዜ ከአገልግሎት ያራቃቸው ምን እንደሆነ ሲጠየቁ ሥራ ማጣት እንደ ምክንያት ሲያቀርቡ ቢደመጡም ሥራ ካገኙም በኋላ ከቤተ ክርስቲያን የሚርቁ ብዙዎች ናቸው፡፡

የአገልግሎት ዓላማና ግብ ምን እንደሆነ የገባቸው ግን ከፊት ይልቅ በመትጋት በማኅበረ ቅዱሳን፣ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በአገልግሎት ማኅበራት በመሳተፍ የተሰጣቸውን ፀጋ በተግባር ሲያውሉም እንመለከታለን፡፡ በአጠቃላይ ሕይወት ከምረቃ በኋላ በአገልግሎት ከፊት ይልቅ በመትጋት ለሌሎች ምሳሌ መሆን የሚችሉ አገልጋዮችም ለቤተ ክርስቲያን ማትረፍ ተችሏል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን ተቀዳሚ ዓላማም ራሱን በክርስትና በማነጽ፣ ለአገልሎት በመትጋት ለቤተ ክርስቲያን ተስፋ የሚሆናትን ትውልድ ማፍራት ነውና፡፡

፫. ጋብቻ፡-

“መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር ነው” እንዲል (ዕብ. ፲፫፥፬) የሰው ልጆች በእግዚአብሔር ከተሰጣቸው ፀጋዎች አንዱ ጋብቻ ነው፡፡ ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉዋት እንደተባለ ከግቢ ጉባኤ በኋላ ይርዘምም ይጠር ወደ ጋብቻ የመግባት ዕድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ጊዜአቸውን በአግባቡ በመጠቀም ለትዳራቸው፣ ለቤተሰባቸው፣ ለማኅበራዊ ሕይወት፣ እንዲሁም ለአገልግሎት በመመደብ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በሰበካ ጉባኤና በመሳሰሉት በመሳተፍ የድርሻቸውን ለመወጣት ጥረት ያደርጋሉ፡፡ ሁሉንም በአግባቡና በሥርዓቱ በመምራት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጣለችባቸውን ኃላፊነት ለመወጣት ከበፊት ይልቅ ይተጋሉ፡፡ ለትውልድም አርአያ ይሆናሉ፡፡

በሌላው አቅጣጫ ደግሞ ትዳርን እንደ ምክንያት በማቅረብ ከአገልግሎት የሚርቁ እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ይህ እንዳይሆን ትዳር የመጨረሻ ግባቸው ሆኖ እንዳይቀር፣ በአገልግሎት እንዲጸኑ፣ ራሳቸውንም በትምህርት እንዲያሳድጉ፣ በማኅበራዊ ሕይወትም መሳተፍ እንዲያስችላቸው መንገድ ማመቻቸት አስፈላጊ ነው፡፡

አገልግሎት ቢመችም ባይመችም የዘወትር የሕይወት አንድ አካል አድርጎ መመልከት ለዚህም በታማኝትና በቆራጥነት ማገልግል ተገቢ ነው፡፡ ግቢ ጉባኤን በትምህርት ላይ ሳሉ ከዓላማቸው እንዳይዘናጉ ማድረጊያ መንገድ እንደሆነ ብቻ በማሰብ ለመሳተፍ መወሰን እንደ ግብ አድርገው የሚያገለግሉ እንዳሉ የሚታወቅ ቢሆንም ተመርቀው ሲወጡ ቢያንስ ለራሳቸው ጥሩ ክርስቲያን ሆነው እንዲገኙ ማደረጉ አንዱ መልካም ነገር ነው፡፡

፬. ማኅበራዊ ሕወት፡-

ከትምህርት በኋላ በማኅበራዊ ሕይወት መሳተፍ የማይቀር ጉዳይ ነው፡፡ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሳሉ ትምህርትና አገልግሎት ብቻ ነበር ትኩረት የሚያደርጉት፡፡ ከግቢ ሲወጡ ግን  ከጠባቡ ዓለም ወደ ሰፊው ዓለም የሚሰማሩ በመሆኑ ዓለም በሯን ከፍታ ትጠብቃቸዋለች፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዱ በማኅበራዊ ሕይወት መሳተፍ ነው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በሠርግ፣ በለቅሶ፣ የተጣላ በማስታረቅ፣ ከወዳጆች ጋር የሕይወት ልምድ መለዋወጥ፣ በአጠቃላይ ያሉበት ማኅበረሰብ የሚኖረውን ኑሮ የመጋራት ሁኔታ ይፈጠራል፡፡

በዚህ ወቅት በተረጋጋና በሰከነ መንፈስ ለእያንዳንዱ ነገር ትኩረት በመስጠት ሕይወትን መምራት ያስፈልጋል፡፡ በእነዚህ ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ምክንያት አገልግሎትን እርግፍ አድርጎ መተው ሳይሆን ቅድሚያ የሚሰጡትን በማስቀደም መትጋት ይገባል፡፡

ዓለም ሰፊ ናት፣ ቀዳዳዎቿም ብዙ ናቸው፡፡ በዚህ ውስጥ ቀልጦ መቅረት ሳይሆን በማስተዋል ሁሉንም በአግባቡና በሥርዓቱ መምራት ተገቢ ነው፡፡

ማጠቃለያ፡-

የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ከተመረቁ በኋላ ሕይወታቸውን እንዴት መምራት እንደሚገባቸው ቆም ብለው ማሰብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በተለይም ለመንፈሳዊ ሕይወት ትልቁን ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል፡፡ የሚሠሩት ሥራ፣ የሚመሠርቱት ጋብቻ፣ ማኅበራዊ ሕይወት እና የመሳሰሉ ገዳዮች ከመንፈሳዊነት እንዳያስወጣቸው ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ይገባል፡፡ አንድ ጊዜ ከአገልግሎት በተለይም ከቤተ ክርስቲያን ከራቁ በኋላ ለመመለስ ሲቸገሩ ማየት የተለመደ በመሆኑ ወደዚህ የሕይወት አቅጣጫ እንዳያመሩ ማእከላት፣ ወረዳ ማእከላት፣ ግንኙነት ጣቢያዎች ክትትል የመድረግ፣ የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር በመፍጠር ማበርታት ይገባል፡፡

ዓለም ከመንፈሳዊ ሕይወት እንድንወጣ በሯ ወለል አድርጋ ስለምትቀበለን የሚያቀርብልንን   ሁሉ ወርቅ መስሎን ለመዝገን ከመሮጥ መቆጠብ፣ ክፉንና ደጉን የምንለይበት አእምሮ ተሰጥቶናልና ልናመዛዝን ይገባል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዝሙሩ ዴማስ ዓለምን ናፍቆ ጥሎት እንደሄደ ሲገልጽ በሐዘን ነው፡፡ “ዴማስ ይህን የዛሬውን ዓለም ወድዶ እኔን ተወኝ ወደ ተሰሎንቄም ሄደ” እንዲል(፪ኛ ተሰ.፬፥፲)፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ዋስ ጠበቃ ይሆናሉ ተብለው ታስበው ነገር ግን ዓለም ጠልፋ የጣለቻቸው ብዙዎች እንዳሉ ተገቢ ነው፡፡ ስለዚህ ከግቢ ጉባኤ ተመርቀን ስንወጣ አንደ ክርስቲያን ማሰብ፣ መኖርን፣ በአገልግሎት መሳተፍን እንደ ዓላማ አድርገን ልንወጣ ያስፈልጋል፡፡ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ከልጆቿ ብዙ ትጠብቃለችና ድምጿን ለመስማት፣ የሰማነውንም ለመተግበር መፋጠን ከትውልዱ ይጠበቃል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጽንሰታ ለማርያም

ነሐሴ ፯ ቀን እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤልን ወደ ከበረና ከፍ ከፍ ወዳለ ጻድቅ ኢያቄም ላከው፡፡ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ፅንሰቷንና ልደቷን በእርሱም ለዓለሙ ሁሉ ድኅነትና ተድላ ደስታ እንደሚሆን ነገረው፡፡

ይህ ጻድቅ ሰው ኢያቄምና የከበረች ሚስቱ ሐና ልጅ ሳይወልዱ ሸመገሉ፡፡ የከበረች ሐና መካን ሁናለችና ስለዚህም እጅግ ያዝኑ ነበር፤ የእስራኤል ልጆች ልጅ ያልወለደውን ከእግዚአብሔር በረከትን ያጣ ነው እያሉ ያቀልሉት ነበርና፡፡ እነርሱም ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ዘወትር ፈጽሞ ይለምኑ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ ወንድ ልጅን ወይም ሴት ልጅን ቢወልዱ ለእግዚአብሔር ቤት አገልጋይ ሊያደርጉት ስዕለትን ተሳሉ፡፡ የልቡናቸውን መሻት የሆነውን ልጅ እንዲሰጣቸው እግዚአብሔርን ዘወትር በቤተ መቅደስ ተገኝተው ዕንባቸውን እያፈሰሱ መማጸናቸውን አላቋረጡም፡፡

ከዕለታት በአንድ ቀንም የከበረ ኢያቄምም በተራራ ላይ ሳለ ሲጸልይና ሲማልድ እነሆ እንቅልፍ እንቅልፍ ብሎት ተኛ፡፡ ያን ጊዜ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ተገለጸለት፡፡ እንዲህም አለው፡- “ሚስትህ ሐና ትፀንሳለች ዓለም ሁሉ ደስ የሚሰኝባትን የብዙዎችም ዐይነ ልቡናቸው በእርሷ የሚበራላቸውን በእርሷም ድኅነት የሚሆንባትን ሴት ልጅን ትወልድልሃለች” አለው፡፡

ሐናም በበኩሏ “አቤቱ ጌታዬ የአባቶቼ የእስራኤል አምላክ እኔ ባርያህ እለምንሃለሁ፤ ስማኝ ለዓይኔ ማረፊያ ለልቤ ተስፋ የምትሆነኝ የተባረከች ሴት ልጅ የማኅፀኔን ፍሬ ስጠኝ” ብላ ስትለምን ዋለች፡፡ ርግብ ከልጆቿ ጋር ስትጫወት ዓይታም በተሰበረ ልብ ውስጥ ሆና “አቤቱ ጌታዬ ለዚች ግእዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሳኸኝ?” ብላ ምርር ብላ አለቀሰች፡፡

ሐና እና ኢያቄም ከካህኑ ዘካርያስ ዘንድ ሄደው “አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሔርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን፤ ሴት ልጅም ብንወልድ ማይ(ውኃ) ቀድታ፣ መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ፣ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን” ብለው ስዕለት ገቡ፡፡ ካህኑ ዘካርያስም “እግዚአብሔር ጸሎታችሁን ይስማችሁ፤ ስዕለታችሁን ይቀበልላችሁ፤ የልቡናችሁን መሻት ይፈጽምላችሁ” ብሎ ቡራኬ ሰጥቶ ሸኛቸው።

ሐና እና ኢያቄም ዕለቱን ራእይ ዓይተው አደሩ፡፡ ራእዩም እንዴት ነው ቢሉ፡- ኢያቄም ፯ቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ርግብ ወርዳ በሐና ራስ ላይ ስታርፍ፤ በጆሮዋም ገብታ በማኅፀኗ ስትተኛ አየ፡፡ ሐናም የኢያቄም መቋሚያ ለምልማ አፍርታ ፍጥረት ሁሉ ሲመገባት አየች፡፡ ከዚህም በኋላ ኢያቄም ያየውን ራእይ ለሐና፣ ሐና ያየችውን ራእይ ደግሞ ለኢያቄም በመንገር ራሳቸውን እግዚአብሔር ለገለጸላቸው ነገር ለማዘጋጀት ተስማሙ፡፡

ሁለቱም በአንድ ልብ ሆነው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም፤ ፈቃደ እግዚአብሔር ቢሆን ነው ብለው “አዳምንና ሔዋንን ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት ብሎ ያበሰረ አምላክ ለኛስ ይልክልን የለምን?” ብለው ዕለቱን መኝታ ለይተው እስከ ፯ ቀን ድረስ ሰነበቱ፡፡ ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ “ከሰው የበለጠች፤ ከመላእክት የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላችሁ” ብሎ ለሐና ነገራት፡፡

በፈቃደ እግዚአብሔር፣ በብሥራተ መልአክ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም ነሐሴ ፯ ቀን ተፀነሰች፡:

ቅዱስ ያሬድ “ማርያምሰ ተኀቱ እምትካት ውስተ ከርሱ ለአዳም ከመ ባሕርይ ጸዓዳ፤ ማርያምስ ከጥንት ጀምሮ በአዳም ባሕርይ ውስጥ እንደ ነጭ ዕንቁ ታበራለች” በማለት እንደተናገረው እግዚአብሔር ቅድስት ድንግል ማርያምን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ድኅነት መሠረት እንዳደረጋት፣ ሊመረመር በማይችል ጥበቡም እንዳዘጋጃት ተናግሯል፡፡ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ “ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤   በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ” ብሎ አመስግኗታል፡፡

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን መሠረት አድርጋ ዕለቱን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምልጃዋ በረከቷ በሁላችን ላይ ይደር፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስንክሳር ነሐሴ ቀን

በፍልሰታ ለማርያም ጾም በቅዳሴ የሚነበቡ ምንባባት፣ ምስባክ እና ቅዳሴ

ምንጭ፡- ግጻዌ

ቀን የመልእክታት

ምዕራፍ እና ቁጥር

ምንባባት ምስባክ ወንጌል ቅዳሴ
ነሐሴ ፩ . ፩ኛ ጢሞ. ፭፥፩-፲፩

 

. ፩ኛ ዮሐ. ፭፥፩-፮

 

. ሐዋ. ፭፥፳፮-፴፬

 

 

. “ሽማግሌዎችን አትንቀፍ …”

 

. “ኢየሱስ መሲሕ እንደሆነ …”

 

. “ከዚህም በኋላ  የቤተ መቅደሱ  ሹም ከሎሌዎቹ ጋር …”

 

. መዝ. ፩፻፲፰፥፵፯-፵፰

 

. አነብብ ትእዛዝከ ዘአፍቀርኩ ጥቀ፤ ወአነሥእ እደውየ ኀበ ትእዛዝከ ዘአፍቀርከ

 

 

 

 

.ዮሐ. ፲፱፥፴፰- ፍጻሜው

 

“ከዚህም በኋላ አይሁድን ስለፈራ በስውር የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር የነበረው የአርማትያስ ሰው …”

 

 

 

. ዘዮሐንስ አፈ ወርቅ አው ዘእግዝእትነ

ነሐሴ ፪ . ፩ኛ ጢሞ. ፪፥፰-ፍጻሜው

 

. ፩ኛ ጴጥ. ፫፥፩-፯

 

. ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

. “እንደ ሰውም ሆኖ ራሱን አዋረደ፤ ለሞት እሰከ መድረስም ታዘዘ…”

 

. “እንዲሁ እናንተ ሚስቶች ሆይ …”

 

. “በሰንበት ቀንም ከከተማው በር ወደ ባሕሩ ዳር ወጣን …”

.መዝ. ፵፬፥፲፬-፲፭

 

. ወይወስዱ ለንጉሥ ደናግለ ድኀሬሃ፤ ወቢጻሂ ይወስዱ ለከ፤ ወይወስድዎን በትፍስሕት ወበሐሴት

ዮሐ. ፰፥፩-፲፪

 

. “ጌታችን ኢየሱስም ወደ ደብረ ዘይት ሄደ፡፡ …”

 

 

. ዘእግእዝእትነ (ጐሥዓ)

ነሐሴ ፫ . ፩ኛ ተሰ. ፫፥፩- ፍጻሜ

 

. ፩ኛ ጴጥ. ፫፥፲-፲፭

 

 

. ሐዋ. ፲፬፥፳- ፍጻሜ

.”መታገሥ ስለተሳነንም ብቻችንን በአቴና ልንኖር ወደድን …”

 

.”ሕይወትን የሚወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚሻ …”

 

. “ደቀ መዛሙርቱም ከበቡት፤ ነገር ግን …”

መዝ. ፵፬፥፲፪-፲፫

 

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ ለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን

. ሉቃ. ፲፰፥፱-፲፰

 

.”ራሳቸውን ለሚያመጻድቁና ባልንጀራቸውን ለሚንቁ እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፤ …”

 

 

. ዘእግእዝእትነ (ጐሥዓ)

ነሐሴ ፬ . ሮሜ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ

 

. ፩ኛ ጴጥ. ፭፥፮-፲፪

 

. ሐዋ. ፲፯፥፳፫-፳፰

 

. “ክፉ ላደረገባችሁም ክፉ አትመልሱለት …”

 

. “እንግዲህ በጎበኛችሁ ጊዜ …”

 

. “በዚህም ሳልፍ ‘ለማይታወቅ አምላክ’ የሚል ጽሕፈት ያለበትን …”

መዝ. ፳፥፩-፪

 

. እግዚኦ በኃይልከ ይተፌሣሕ ንጉሥ፤ ወብዙኃ ይተሐሠይ በአድኅኖተከ ፍተወተ ነፍሱ ወሐብኮ”

. ሉቃ. ፲፬፥፴፩-ፍጻሜ

 

. ንጉሥም ሌላውን ንጉሥ ይወጋ ዘንድ ሊሄድ ቢወድ ሁለት እልፍ ይዞ …”

 

 

. ዘእግእዝእትነ አው ዘቄርሎስ

ነሐሴ ፭ . ፪ኛ ቆሮ. ፲፪፥፲-፲፯

 

 

. ፩ኛ ዮሐ. ፭፥፲፬-ፍጻሜ

 

 

. ሐዋ. ፲፭፥፩-፲፫

. “ስለዚህም ስለ ክርስቶስ መከራ መቀበልን፣ መሰደብን፣ መጨነቅን…”

 

. “ በእግዚአብሔር ዘንድ ያለችን መወደድ ይህች ናት …”

 

. “ከይሁዳ ሀገርም የወረዱ ሰዎች…”

. መዝ. ፲፯፥፵፫

 

. ወትሰይመኒ ውስተ ርእሰ ሕዝብ፤ ሕዝብ ወኢየአመር ተቀንየ ሊተ፤ ውስተ ምስማዐ ይዝን ተሠጥዉኒ

ሉቃ. ፲፭፥፩-፲፩

 

. “ቀራጮችና ኀጢአተኞችም ሊሰሙት ወደ እርሱ ይቀርቡ ነበር፡፡”

 

 

 

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ ፮ . ፩ኛ ቆሮ. ፫፥፲-፳፪

 

. ፩ኛ ጴጥ. ፫፥፩-፯

 

 

.ሐዋ. ፲፮፥፲፫-፲፱

. “እግዚአብሔር እንደ ሰጠኝ ጸጋ መጠን እንደ ጠራቢዎች …”

 

. እንዲሁ እናንተ ሚስቶች ሆይ …”

 

. በሰንበት ቀንም ከከተማው በር ወደ ባሕሩ ዳር ወጣን …”

መዝ. ፵፬፥፲፪-፲፫

 

. ወይሰግዳ ሎቱ አዋልደ ጢሮስ በአምኃ ለገጽኪ ይትመሐለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን

ማር. ፲፮፥፱-፲፱

 

. በእሑድ ሰንበትም ማለዳ ተነሥቶ ሰባት አጋንንትን ..”

 

 

. ዘእግዝእትነ አው ግሩም

ነሐሴ ፯ . ማቴ. ፩፥፩-፲፯

 

. ዕብ. ፱፥፩-፲፩

 

 

. ፩ኛ ጴጥ. ፪፥፮-፲፰

 

 

 

. ሐዋ. ፲፥፩-፴

. “የዳዊት ልጅ የአብርሃም ልጅ፤ …”

 

. “ፊተኛይቱም ደግሞ የአገልግሎት ሥርዓትና የዚህ ዓለም …”

 

. “እንዲህ ተጽፎልናል፤ “እነሆ በጽዮን የተመረጠውንና የከበረውን …”

 

. “በቂሣርያም ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፣ …”

.  ዘነግህ፡- መዝ. ፹፮፥፩-፪

 

. መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን፣ ያበድሮን እግዚአብሔር ለአናቅጸ ጽዮን እም ኵሉ ለዐይኒሁ ለያዕቆብ

 

 

 

. መዝ. ፺፫፥፲፪

 

. ብፁዕ ብእሲ ዘአንተ ገሠጽከ እግዚኦ ወዘመሀርኮ ሕገከ፤ ከመይትገኀሥ እመዋዕለ እኩያት

. ማቴ. ፲፮፥፲፫-፳፬

 

. “ጌታችን ኢየሱስም ወደ ፊለረጶስ ቂሣርያ አገር በደረሰ ጊዜ …”

 

 

 

. ዘእግእዝእትነ (ጐሥዓ)

ነሐሴ ፰ . ሮሜ. ፱፥፳፬-ፍጻሜ

 

. ፩ኛ ጴጥ. ፬፥፲፪- ፍጻሜ

 

. ሐዋ. ፲፮፥፴፭-ፍጻሜ

. “ወደ ክብሩ የጠራንና የሰበሰበንም እኛ ነን፤…”

 

. “ወዳጆች ሆይ በእናነተ መካከል እንደ እሳት ሊፈትናችሁ …”

 

. “በነጋ ጊዜም ገዢዎቹ “እነዚያን ሰዎች ፈትታችሁ ልቀቋቸው” …”

. መዝ. ፶፯፥፹፮

 

. ወድቀት እሳት ወኢርክዋ ለፀሐይ፡ ዘእነበለ ይትዐወቅ ሦክክሙ ሕለተ ኮነ ከመ ሕያዋን በመዓቱ ይውኀጠክሙ

. ማቴ. ፯፥፲፪-፳፮

 

. “ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትወዱትን ሁሉ እናንተም፤ …”

 

. ዘእግእዝእትነ (ጐሥዓ)

ነሐሴ ፱ . ፊልጵ. ፩፥፲፪-፳፬

 

 

. ፪ኛ ዮሐ. ፩፥፮-ፍጻሜ

 

. ሐዋ. ፲፭፥፲፱-፳፭

 

 

. “ወንድሞች ሆይ ይህ የደረሰብኝ በእውነት ወንጌልን …”

 

. “ፍቅራችንም ይህች ናት፤ በእግዚአብሔርም ትእዛዝ …”

 

. “ሁላችን ከተሰበሰብን በኋላ በአንድ ቃል …”

. መዝ. ፵፬፥፱

 

. ወትቀውም ንግሥት በየማንከ

በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወሑብርት

 

. ዮሐ. ፲፥፩-፳፪

 

. “እውነት አውነት እላችኋለሁ ወደ በጎች ስፍራ በበሩ …”

 

 

. ዘእግዝእትነ አው ባስልዮስ

ነሐሴ ፲ . ዕብ. ፲፪፥፳፪-ፍጻሜ

 

. ፩ጴጥ. ፩፥፮-፲፫

 

 

. ሐዋ. ፬፥፴፩-ፍጻሜ

 

. “እናንተ ግን የሕያው የእግዚአብሔር ከተማ ወደምትሆን …”

 

. “እስከ ዘለዓለም ደስ ይላችኋል ነገር ግን በሚመጣባችሁ ልዩ ልዩ መከራ …”

 

. “ሲጸልዩም በአንድነት ተሰብስበው …”

. መዝ.፥፸፫፥፪

 

. ተዘከር ማኅበርከ ዘአቅደምከ ፈጢረ፤ ወአድኀንከ በትረ ርስትከ ደብረ ጽዮን ዘኀደርከ ውስቴታ

. ሉቃ. ፲፮፥፱-፲፱

 

. እኔም እላችኋለሁ፤ በላቀባችሁ ጊዜ እነርሱ በዘለዓለም ቤታቸው …”

 

 

 

. ዘእግእዝእትነ (ጐሥዓ)

ነሐሴ ፲፩ . ፩ኛ ቆሮ. ፭፥፲፩-ፍጻሜ

 

. ፩ዮሐ. ፪፥፲፬-፳

 

 

 

. ሐዋ. ፲፪፥፲፰-ፍጻሜ

. “አሁንም ከወንድሞች መካካል ዘማዊ ወይም ገንዘብን የሚመኝ፣ …”

 

. አባቶች ሆይ በመጀመሪያ የነበረውንዐውቃችሁታልና እጽፍላችኋለሁ …”

 

. “በነጋ ጊዜ ወታደሮች “ጴጥሮስ ምን ሆነ?” ብለው ጠየቁ …”

. መዝ. ፵፬፥፲፮-፲፯

 

. ህየንተ አበውኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ ወትሠዩሚዮሙ መላእከተ ለኵሉ ምድር ወይዘክሩ ስመኪ በኵሉ ትውልደ ትውልድ

. ሉቃ. ፮፥፳-፥፳፬

 

. “እርሱም ወደ ደቀ መዛሙርቱ ዐይኖቹን አንስቶ እንዲህ አላቸው፡- “እናንተ ድሆች ብፀዓን ናችሁ …”

 

 

. ዘእግእዝእትነ (ጐሥዓ)

 

ነሐሴ ፲፪ . ፩ቆሮ. ፱፥፲፯-ፍጻሜ

 

 

. ይሁ.፩፥፰-፲፬

 

 

 

. ሐዋ. ፳፬፥፩-፳፪

. “ይህንስ በፈቃዴ አድርጌው ብሆን ዋጋዬን ባገኘሁ ነበር፤ በግድ ከሆነ ግን በተሰጠኝ መጋቢነት አገልግላለሁ …”

 

. “እንዲሁም እነዚህ ሰዎች ደግሞ በሕልማቸው ሥጋቸውን ያረክሣሉ …”

 

. “በአምስተኛውም ቀን ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ ከመምህራኑና ጠርጠሉስ ከሚባል አንድ ጠበቃ …”

. ዘነግህ ምስባክ፡- መዝ. ፩፻፴፯፥፩-፪

 

.  በቅድመ መላእክቲከ እዜምር ለከ ወእሰግድ ውስተ ጽርሐ መቅደስከ ወእገኒ ለስምከ

 

. መዝ. ፸፩፥፩-፪

 

. እግዚኦ ኵነኔከ ሀቦ ለንጉሥ፤ ወጽድቀከኒ ለወልደ ንጉሥ፤ ከመ ይኰንኖሙ ለሕዝብከ በጽድቅ

. ማቴ. ፳፭፥፴፩-ፍጻሜ

. “የሰው ልጅ በጌትነቱ በቅዱሳን መላእክትን ሁሉ አስከትሎ …”

 

 

.ማቴ. ፳፪፥፩-፲፭

 

. “ጌታችን ኢየሱስ ዳግመኛ መልሶ በምሳሌ ነገራቸው፤ …”

 

 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈ ወርቅ

ነሐሴ ፲፫ . ዕብ. ፲፩፥፳፫-፴

 

 

. ፪ኛ ጴጥ. ፩፥፲፭-ፍጻሜ

 

. ሐዋ. ፯፥፵፬-፶፩

. “ሙሴ በተወለደ ጊዜ በእምነት ሦስት ወር በአባቱ ቤት ሸሸጉት …”

 

. “ነገር ግን የጠራችሁ ቅዱስ እንደሆነ እንዲሁ እናንተም …”

 

. “ሙሴን ተናግሮ እንዳዘዘው በአሳየው ምሳሌ የሠራት የምስክር ድንኳን በአባቶቻችን ዘንድ …”

. ነግህ ምስባክ፤ መዝ. ፷፱፥፲፭-፲፮

 

. ደብር ርጉዕ ወደብር ጥሉል፤ ለምንት ይትነሥኡ አድባርርጉዓን፤ ደብር ዘሠምሮ እግዚአብሔር ይኀድር ውስቴቱ

 

 

. መዝ. ፹፰፥፲፪-፲፫

. ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ ወይሴብሑ ለስምከ መዝራዕትከ ምስለ ኃይል

. ማቴ. ፲፯፥፩-፲፬

. “ከስድስት ቀንም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ወንድሙ ዮሐንስን …”

 

 

 

 

. ሉቃ. ፱፥፳፰-፴፰

 

. “ከዚህም ነገር በኋላ በስምንተኛው ቀን ጌታችን ኢየሱስ …”

 

 

 

 

. ዘእግዝእትነ አው ዘዲዮስቆሮስ

ነሐሴ ፲፬ . ፩ኛ ቆሮ. ፩፥፲-፲፱

 

 

 

. ያዕ. ፩፥፲፪-፳፬

 

 

 

. ሐዋ. ፲፥፴-፵፬

. “ወንድሞቻችን አንድ ቃል እንድትናገሩ እንዳታዝኑ፣ ፍጹማንም እንድትሆኑ …”

 

. “መከራን የሚታገሥ ሰው ብፅ ነው፤ ተፈትኖ እግዚአብሔር  ለሚወዱት ተስፋ ያደረገላቸውን …”

 

. “ቆርኔሌዎስም እንዲህ አለው፤ “የዛረ አራት ቀን በዘጠኝ ሰዓት በዚች ሰዓት በቤቴ ስጸልይ …”

. መዝ. ፵፫፥፬-፭

 

. ዘእዘዝከ መድኃኒቶ ለያዕቆብ፤ ብከ ንወግዖሙ ለኵሎሙ ፀርነ ወበስምከ ነኃሥሮሙ ለእለ ቆሙ ላዕሌነ

. ማቴ. ፲፯፥፲፬-፳

 

. “ወደ ሕዝቡም በደረሱ ጊዜ አንድ ሰው ወደ እርሱ ቀርቦ እየለመነ ሰገደለት …”

 

 

ዘእግዝእትነ አው ዘዮሐንስ አፈ ወርቅ

   

 

 

ጾመ ፍልሰታ ለማርያም

ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎቻችንና ለመላው ኦርቶዶክሳውያን፤

እንኳን ለፍልሰታ ማርያም ጾም በሰላም አደረሳችሁ!

አምላክን የወለደች እመቤታችን ድንግል ማርያም ከዕረፍቷ በኋላ ከእርሳቸው ስለመለየቷ ሐዋርያት ፈጽሞ እያዘኑ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ተገለጠላቸው፤ እርሷን በሥጋ ያዩ ዘንድ እንዳላቸውም ተስፋ ሰጣቸው፡፡

ወንጌላዊ ዮሐንስም እስያ በሚባል አገር እያስተማረ ሳለ በነሐሴ ወር ዐሥራ ስድተኛ ቀን ተድላ ደስታ ወደአለባት ገነት በመንፈስ ቅዱስ ተነጠቀ፡፡ የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን የእመቤታችን ማርያም ሥጋዋ ካለበት ከዕፀ ሕይወት ዘንድ ተቀምጦ አየው፡፡ የንጽሕት እናቱንም ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሩዋት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው፤ እነርሱም ”የንጽሕት እናቱን ሥጋ ታወጪ ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል‘ አሏት፡፡ያን ጊዜም ከዕፀ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን ማርያም ሥጋዋ ወጣ፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችንም እንዲህ እያለ አረጋጋት፤ ”የተወደድሽ የወለድሽኝ እናቴ ሆይ ዘላለማዊ ወደ ሆነ መንግሥተ ሰማያት አሳርግሽ ዘንድ ነዪ፡፡‘ ያን ጊዜም በገነት ያሉ ዕፅዋት ሁሉም አዘነበሉ፤ መላእክት፤ የመላእክት አለቆች ጻድቃን ሰማዕታትም እየሰገዱላትና ፈጽሞ እያመሰገኗት አሳረጓት፡፡ አባቷ ዳዊትም ንግሥት እመቤታችን ወረቀ ዘቦ ለብሳ ደርባ ደራርባ በቀኝህ ትቀመጣለች እያለ በበገና አመሰገናት፡፡ በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጣ ከዐረገች በኃላ በልጆችዋና በፈጣሪዋ ቀኝ በታላቅ ክብር ተቀመጠች፡፡ ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ሰግዶላት ተመልሶ ከሰማይ ወረደ፤ ሐዋርያትን ተሰብስበው ስለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ፈጽሞ ሲያዝኑና ሲተክዙ አገኛቸው፡፡ እርሱም እንዳየ እንደሰማ ሥጋዋንም በታላቅ ክብር በምስጋና እንዳሳረጓት ነገራቸው፡፡ ሐዋርያትም በሰሙ ጊዜ ዮሐንስ እንዳየና እንደሰማ ባለማየታቸውና ባለመስማታቸው እጅግ አዘኑ፡፡ ከዚህም በኋላ እያዘኑ ሳሉ እነሆ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠላቸውና ”የፍቅር የአንድነት ልጆች ሰላም ይሁንላችሁ፤ ስለ እናቴ ማርያም ሥጋ ለምን ታዝናላችሁ፡፡ እነሆ እኔ እርስዋን በሥጋ ላሳያችሁ ልባችሁም ደስ ሊለው ይገባዋል‘ አላቸው፡፡ ይህንንም ብሎ ከእርሳቸው ዘንድ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

ሐዋርያትም ዓመት ሙሉ ቆዩ፤ የነሐሴም ወር በባተ ቀን ለሐዋርያት ዮሐንስ እንዲህ አላቸው፡፡ ”አምላክን የወለደች የእመቤታችንን ሥጋዋን ለማየት የተዘጋጀን አድርጎ ያሳየን ዘንድ ኑ ይህን ሁለት ሱባዔ በጾም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው” በልጅዋ በወዳጅዋ ቀኝ ተቀምጣ አይተን በእርሷ ደስ እንዲለን፡፡‘

በዚያን ጊዜም ዮሐንስ እንዳላቸው በጾም በጸሎት ሱባዔ ያዙ፤ የነሐሴ ወር እንደዛሬ ዐሥራ ስድስተኛ ቀን በሆነ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉንም ሐዋርያት ወደ ሰማይ አወጣቸው፡፡ በታላቅ ክብር በተወደደ ልጅዋ ቀኝ ተቀምጣ ከሥጋዋ ተዋሕዳ ተነሥታ እመቤታችን ማርያምን አዩዋት፡፡ እጆቿንም ዘርግታ የከበሩ ሐዋርያትን እያንዳንዳቸውን ባረከቻቸው፤ በልባቸውም እጅግ ደስ አላቸው፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በከበረ ሥጋውና ደሙ ላይ ሠራዔ ካህን ሆነ፡፡ እስጢፋኖስም አዘጋጀ፤ ዮሐንስም ”በመፍራት ቁሙ‘ አለ፡፡ ሁሉም ሐዋርያት በመሰዊያው ዙሪያ ቆሙ፤ በዚያን ጊዜ ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ ታላቅ ደስታ ሆነ፡፡ ጌታችንም የቅዳሴውን ሥርዓት በፈጸመ ጊዜ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው፡፡

ከዚያም በኪሩቤልና በሱራፌል ሠረገላ ተቀምጣ በምታርግ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱን እመቤታችን ማርያምን እንዲህ ብሎ ተናገራት፡፡ ”በዚች ቀን የሆነ የዕርገትሽን መታሰቢያ በዓለም ውስጥ እንዲሰበኩ ልጆችሽ ሐዋርያትን እዘዣቸው፡፡ መታሰቢያሽን የሚያደርገውን ሁሉ ተጠብቆም በዚች ቀን ቅዱስ ቁርባን የሚቀበለውን ኃጢአቱን እደመስስለታለሁ፡፡ የእሳትን ሥቃይ ከቶ አያያትም፤ መታሰቢያሽን ለሚያደርግ ሁሉ በዚች ቀን ለድኆች በስምሽ ለሚመጸውት ቸርነቴ ትገናኘዋለች፤ ይህም ሥጋሽ ወደ ሰማይ ያረገበት ነው፡፡‘

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ክብር ይግባውና ጌታችንን እንዲህ አለቸው፤ ”ልጄ ሆይ እነሆ በዓይኖቻቸውም አዩ፤ በጆሮዎቻቸውም ሰሙ፤ በእጆቻቸው ያዙ ሌሎችም ታላላቅ ድንቆች ሥራዎችን አዩ፡፡‘ እመቤታችንም ይህን ስትናገር ጌታችን ሰላምታ ሰጥቷቸው በታላቅ ደስታ ወደ ደብረ ዘይት ተመለሱ፡፡

የተወደዳችሁ ወንድሞች ሆይ! ይህን ጾም ልንጾምና በፍጹም ደስታ የእመቤታችንን መታሰቢያዋን እናደርግ ዘንድ ይገባናል፡፡ እርሷ ስለ እኛ ወደተወደደ ልጅዋ ሁልጊዜ ትማልዳለች፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን፡፡ በረከቷም ሐዋርያት በሰበሰበዋት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ከሁላችን ጋር ይሁን፤ ለዘላለሙ አሜን፡፡

ከመጽሐፈ ስንክሳር፣ ነሐሴ ፲፮

የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር የከሰዓት በኋላ ውሎ

የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ከሰዓት በኋላ ውሎው የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎችን በማስተናገድ ላይ ይገኛል፡፡

በዚህ ጉባኤ ላይ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ(ዾ/ር) የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ የኒውዮርክ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን መልእክታቸውንም አስተላልፈዋል፡፡ በመልእክታቸውም ትምህርት ሦስት መሠረታዊ ነገሮችን መያዝ እንዳለበትም ጠቅሰዋል፡፡ እነዚህም፡-  ትምህርት መንፈሳዊ ሀብት መሆኑ፤ ትምህርት ብርሃን እንደሆነ፤ እንዲሁም ትምህርት የማያልቅ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

“ትምህርት መንፈሳዊ ሀብት ነው ስንል አይሰረቅም፣ አይወሰድም፣ አይሞትም፣ ለሌላው የሚያካፍሉትና የሚቀጥል ነው፡፡” ብለዋል፡፡

ብፀዕነታቸው የትምህርት ብርሃንነትን ሲገልጹም “ትምህርት ብርሃን ነው፡፡ ፊትህን፣ ጎንህን፣ ኋላህን እንድታይና እንድታስተውል ነው የሚያደርገው፡፡ ዕውቀታቸውን በመንፈሳዊው የሕይወት ጎዳና ላይ ያደረጉ ሰዎች ብሩሀን ናቸው” ሲሉ የትምህርትን ብርሃንነት ጠቅሰዋል፡፡

ብፁዕነታቸው መንፈሳዊው ትምህርት የማያልቅ መሆኑን ሲያብራሩም “መንፈሳዊ ትምህርት አይልቅም፤ እግዚአብሔርንም አጥንተን አንጨርሰውም፡፡ ትምህርት ትዕግሥትን፣ ጊዜን፣ … ይጠይቃል” በማለት በሴሚናሩ ላይ ለተሳተፉ በግቢ ጉባኤ ለተማሩና ተምረው ለወጡ ወጣቶች በተማሩት ትምህርት መንፈሳዊነታቸውን ጠብቀው በቅንነትና በዕውቀት ላይ ተመርኩዘው እንዲያገለግሉ አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

ከብፁዕ አባታችን ምክርና ቡራኬ በኋላ ጥናታዊ ጽሑፎቸ መቅረባቸው የቀጠሉ ሲሆን “የሕይወት ክህሎት” በዶ/ር ወሰን አራጋው፤ እንዲሁም “የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት መልካም ዕድሎች እና ፈተናዎች” በሚል በዲ/ን ብርሃኑ ታደሰ በተከታታይ ቀርበዋል፡፡

ሴሚናሩ እስከ ምሽት የሚቀጥል ሲሆን ተጨማሪ ጥናታዊ ጽሑፎችና ውይይቶች ይካሄዳሉ፡፡

የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ጥናታዊ ጽሑፎች በማቅረብ ቀጥሏል

የግቢ ጉባኤያት ሴሚናር ሐምሌ ፳፫ ቀን ፳፻፲፬ ዓ.ም ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ጀምሮ በመካሄድ ላይ ሲሆን ልዩ ልዩ መርሐ ግብሮች ሰዓታቸውን ጠብቀው እየቀረቡ ይገኛሉ፡፡

በጸሎተ ወንጌል የተጀመረው መርሐ ግብር የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን ያሬዳዊ መዝሙር በማቅረብ ቀጥሎ “ዕውቀት የሕይወት ምንጭ ነው” (ምሳ. ፲፮፥፳፪) በሚል ርእስ ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ያስተማሩ ሲሆን፤ ዲ/ን ዋሲሁን በላይ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ “የማኅበረ ቅዱሳን ታሪክ፣ አገልግሎትና ፈተናዎች ከ፲፱፻፹፬-፳፻፲፬ ዓ.ም” በሚል ሰፋ ያለ ጥናታዊ ጽሑፍ አቅርበዋል፡፡

በጥናታቸውም ለማኅበረ ቅዱሳን መመሥረት ምክንያት የሆኑትን መሠረታዊ ጉዳዮችና ሂደቱን፣ ያለፉትን የ፴ ዓመታት አገልግሎት፣ እንዲሁም ያጋጠሙ ፈተናዎችንና ፈተናዎቹን ለመፍታት የተደረጉ ጥረቶችንም ዳስሰዋል፡፡ ጥናታዊ ጽሑፉ ከቀረበ በኋላም ተሳታፊዎች ላነሷቸው ጥያቄዎች በአቶ ግዛቸው ሲሳይ የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ሰብሳቢ እና ጥናቱን ባቀረቡት ዲ/ን ዋሲሁን በላይ ምላሽ ተሰጥቶባቸው የጉባኤው የጠዋቱ መርሐ ግብር ተጠናቋል፡፡