ወጣትነትና ታማኝ አገልጋይነት

ክፍል አንድ

በዲ/ን ወልደ ቂርቆስ ደሳለኝ

የሰው ልጅ በዚህች ምድር ላይ በሚኖረው ቆይታ ብዙ ኃይልና መነሳሳት የተሞላበት ዘመኑ የወጣትነት ዘመን ነው፡፡ የሰው ልጅ ከሌላው ጊዜ በተለየ አዳዲስ ግኝቶችን ለማበርከት፣ እጅግ ከባድና ውስብስብ የሚመስሉ ጉዳዮችን በድፍረት ለመጀመርና ለመሞከር ታላቅ ወኔና ድፍረት የታጠቀበት ዘመን ቢኖር የወጣትነት ዘመን ነው፡፡ የመመራመር ጉጉት፣ የማወቅ፣ የማገልገል ልዩ ትጋትና ቁርጠኝነትን የተላበሰ ዘመንም የሚታየው በወጣትነት ዘመን ነው፡፡ አካላዊ ማኅበራዊ፣ መንፈሳዊ ብሎም ምጣኔ ሀብታዊ ለውጦች በስፋት የሚስተናገዱበት፣ ውስብስብ ፈተናዎች የሚገጥሙበት ዘመን ቢኖር የወጣትነት ዘመን ነው፡፡ ችኩልነት፣ እብሪተኝነት፣ አልታዘዝ ባይነት የሚፈታተኑት በወጣትነት ዘመን ነው፡፡ ለሉላዊነት አስተሳሰብ፣ ለረቀቀ የቴክኖሎጂ አቅርቦት፣ ለባህል ብረዛ፣ ለሥራ አጥነት፣ ለቤተሰብ ጫና የሚጋለጠውም በወጣትነት ዘመን ላይ ነው፡፡

ይህንን ወጣትነት ብዙዎች እንደተጠቀሙበት ሁሉ ብዙዎችም መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ተብለው “እንግዲህስ ምድራችንን እንዳታቦዝን ቁረጣት” (ሉቃ. ፲፫፥፮) እንደተባለች እንደዚያች በለስ የመቆረጥ ፍርድ ተፈርዶባቸዋል፡፡ በዚህ የወጣትነት ዘመን አቤል የፈጣሪውን ንጽሐ ባህሪይነት ተረድቶ ቀንዱ ያልከረከረውን፣ ጥፍሩ ያልዘረዘረውን፣ ጸጉሩ ያላረረውን ንጹሕ የመሥዋዕት ጠቦት በንጽሕና አቅርቦ ከእግዚአብሔር ዘንድ አትርፏል፡፡ ወንድሙ ቃየልም በንዝህላልነትና ግድየለሽነት ከሕይወት መስመር ወጥቶ ተቅበዝባዥነትን ተከናንቧል፡፡ (ዘፍ.፬፥፫-፲፭)፡፡ በወጣትነት ዮሴፍ እንደ ወርቅ በእሳት ተፈትኖ ንጽሕናውን አሳይቶበታል፤ በዚህ በወጣትነት ራሱን ለታይታና ለይሰሙላ ባልሆነ ፍጹም ትሕትና ከወንድሞቹ ሁሉ በታች ራሱን ዝቅ አድርጎ በንግሥና ከፍ ከፍ ብሎበታል፡፡ (ዘፍ.፴፱፥፩)፡፡ በዚያም በምድርና በሰማይ ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶም ያማረ ፍሬ አፍርቶ ዝገት የማይበላውን፣ ሌቦች የማይሰርቁትን መዝገብ አከማችቶበታል፡፡

በዚሁ የወጣትነት ዘመን እንደ ጢሞቴዎስ ያሉት ትጉሃን ደቀ መዛሙርት በትጋት የመምህራቸውን ፈለግ ተከትለው ለክርስቲያን ወገኖቻቸው ተርፈውበታል፤ በመምህራቸውም እንዲህ ተወድሰዋል”በአንተ ያለው ግብዝነት የሌለበትን እምነትህን አስባለሁ” (፪ጢሞ. ፩፥፲፭)፡፡ በወጣትነት ከሰማያዊው ክብር ይልቅ ወደ ምድራዊው ድሎት የመጡ እነዴማስም እንዲህ ተብለዋል”ዴማስ ይህንን የዛሬውን ዓለም ወድዶ እኔን ተወኝ፤ ወደ ተሰሎንቄም ሄደ” (፪ጢሞ.፬፥፲)፡፡ በዚሁ የወጣትነት ዘመን ነው እንደ ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ያሉት መከራና ግፍን ሳይፈሩ በጥብአትና በእምነት ለታላቅ ድልና መንፈሳዊ አክሊል የበቁት፡፡ እንዲያው በጥቅሉ ይህንን የወጣትነት ዘመን ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ አስገዝተው ለክብር ሞት፣ ለዘለዓለም ሕይወት የበቁ ብዙዎች እንደሆኑ ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፤ አበው ሊቃውንትም ያስተምራሉ፡፡

በውኑ የእኛስ የወጣትነት ዘመን የትጋት ነውን? ከላይ እንደተጠቀሱት ደጋግ አበው ቅዱሳን የተሰጠንን መክሊት ሠርተን፣ ደክመን፣ ወጥተን ወርደን ለማትረፍ የጣርንበት ነው? ወይስ የተሰጠንን ጸጋና መክሊት ቀብረን ያው ያለን እንኳ ተወስዶብን ለቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለት ወደማይጠፋ እሳት ለመጣል እየጠበቅን ነው? በውኑ በወጣትነቱ ደግና ታማኝ አገልጋይ (ገብር ሔር) ማን ነው? ወጣቶች ወደ መንፈሳዊ አገልግሎት እንዳይቀርቡስ እንቅፋት የሆናቸው ምንድን ነው? ተግተው ለአገልግሎት የመጡት ወጣቶችስ እየገጠማቸው ያለው ፈተናና ተግዳሮት ምንድነው? በወጣትነት ታማኝ መንፈሳዊ አገልጋይ ለመሆንስ ምን ማድረግ አለባቸው? የሚሉትን ነጥቦች በዚህ ጽሑፍ ለመዳሰስ እንሞክራለን፡፡ በቅድሚያ ግን ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዳንቀርብ፣ ለማገልገል ዝግጁ እንዳንሆን እንቅፋት የሆኑን ምክንያቶችን በጥቂቱ እንመልከት፡-

የመንፈሳዊ አገልግሎት እንቅፋቶች

በዘመናችን አብዛኛዎቹ ወጣቶች ከእግዚአብሔር ቤት እየሸሹ ውሎና አዳራቸው በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ወደማይጠቀሙበት አቅጣጫ በማምራት ከዓላማቸው ተሰናክለው ለጤና መታወክ በሚያበቋቸው አልባሌ ቦታዎች ይሆናሉ፡፡ ድምጿን ከፍ አድርጋ ለምትጣራ ቤተ ክርስቲያን ልባቸውን ከመስጠት ይዘገያሉ፡፡ ወጣቶች ወደ አገልግሎት እንዳይገቡ እንቅፋት ከሚሆኑ ነገሮች መካከል የሚከተሉትን ጠቅለል አድርገን እንመልከት፡-

፩. ቤተ ክርስቲያንን አለማወቅ

፪. አልችልም/አይገባኝም ማለት

፫.ተነሳሽነት ማጣትና ለነገ ማለት

 ፬. በቀላሉ ተስፋ መቁረጥ

፩. ቤተ ክርስቲያንን አለማወቅ

ብዙ ወጣቶች ስብከተ ወንጌልን ልብ ሰጥቶ ከመታደም፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ጊዜ ሰጥቶ በተመስጦና በጥልቀት አንብቦ ከመረዳት፣ ሊቃውንትን፣ መምህራነ ወንጌልንና ካህናትን ቀርቦ ከመጠየቅ ይልቅ በተለያየ ሰበብና ምክንያት ራሳቸውን ስላሸሹ ቤተ ክርስቲያንን በውል ማወቅ፣ መረዳት ሲከብዳቸው ይስተዋላል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እናውቃለን ብለው የሚያስቡት እንኳን ዓለም ከምታቀርብላቸው ሥጋዊ ፍላጎትን ከሚያነሣሱ ከማኅበራዊ ትስስር ገጾች በለቃቀሟቸውና በቃረሟቸው የተቆራረጡና ምሉእ ያልሆኑ ሕጸጽና ግድፈት ያለባቸውን መረጃዎች በመሰብሰብ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮዋን በውል ተረድተዋል ለማለት ይቸግራል፡፡

በዚህ ጽሑፍ ቤተ ክርስቲያንን አለማወቅ ስንል እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር ፈቃድ፣ የቤተ ክርስቲያንን ዶግማዊና ቀኖናዊ ድንጋጌዎች፣ አካሄዷንና አሠራሯን አለማወቅን ለመግለጽ ነው፡፡

ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን ምንድን ናት? ተልእኮዋስ ምንደነው? ቤተ ክርሴቲያን ከእኔ ምን ትፈልጋለች? እኔስ ከቤተ ክርስቲያን የማገኘው ጥቅም ምንድነው? እነዚህን ለመሰሉ መሠረታዊ ጥያቄዎች ለኅሊናቸው በውል ምላሽ መስጠት ሲቸግራቸው ይስተዋላል፡፡ ለአንዳንድ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን የእነ አቡነ እገሌ፣ አባ እገሌ፣ ሰባኪ (ዘማሪ) እገሌ ናቸው፡፡ እነዚህ ዓይኑንና ተስፋውን የጣለባቸው ሰዎች ፈተና አድክሟቸው የዓለም አንጸባራቂ ውበት ስቦ አታሏቸው እንደ  ዴማስ (፪ጢሞ.፬፥፲) ወደ ኃላ መጓዝ፣ መሰናከል በጀመሩ ጊዜ ቀድሞውኑ ቤተ ክርስቲያንን በእነዚህ ሰዎች ትከሻ ላይ ወስነዋት ነበርና የእነርሱን ድካምና ጥፋት ከቤተ ክርሰቲያን ለይቶ ማየት ያቅታቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ከሕወት መንገድ ተደናቅፈው ይወድቃሉ፡፡

ለዚህም ነው በየአድባራቱ፣ ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶች “የእገሌ መዝሙር ካልተዘመረ፣ እገሌ የተባለ ሰባኪ ካልመጣ፣ አባ እገሌ ካልተሾሙ፣ አቡነ እገሌ ካልተሻሩ አላገለግልም፣ አልመጣም …” ወዘተ በማለት ቀስ በቀስ ከቤተ ክርስቲያን እቅፍ የወጡና እየወጡ ያሉ ምእመናን ቁጥራቸው እየበዛ የመጣው፡፡ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን ከእነዚህ ነገሮች በላይ የሆነች አንዲት፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኩላዊት (ዓለም አቀፋዊት) ናት፡፡ (ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ፤ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት)፡፡ ለዚህም ነው አበው በሃይማኖት ጸሎት ደግመን ደጋግመን እንዘክረው ዘንድ “ከሁሉ በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን” ብለው ያስቀመጡልን፡፡

 ቤተ ክርስቲያንን አለማወቅ በሦስት ክፍሎች ከፍለን ልናየው እንችላለን፡፡

የመጀመሪያው ስለ ቤተ ክርስቲያን ምንም ዓይነት ዕውቀትና ግንዛቤ አለመኖር ነው፡፡ አንዳንድ ወጣቶች ወላጆቻቸው በልጅነታቸው ካመላለሷቸው በኋላ እግሮቻቸው ደጀ ሰላምን አልረገጡም፡፡ ነገር ግን በአንገታቸው ማዕተብ አጥልቀው፣ በስማቸውም ክርስቲያን፣ የክርስቶስ ወገን ተሰኝተዋል፡፡ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ቤተ ክርስቲያን ምን እንደሆነች፣ ተልእኮዋ ምን እንደሆነ፣ በዚህ ወቅት ቤተ ክርስቲያን ምን ሁኔታ ላይ እንደምትገኝ አያውቁም፤ የማወቅ ፍላጎታቸውም የደከመ ነው፡፡ እናም መቼም ቢሆን ውስጣቸው በቤቱ ቅናት ተቃጥሎ “እስመ ቅንዐተ ቤትከ በልዐኒ፤ የቤተህ ቅናት በልቶኛልና” (መዝ.፷፰፥፱) ብለው ለአገልግሎት ይነሡ ዘንድ፣ የሀገር፣ የቤተ ክርስቲያን መጥፋት አሳዝኗቸው ወደ መንፈሳዊ ቁጭት ውስጥ ይገቡ ዘንድ “ኢታርእየነ ሙስናሃ ለኢየሩሳሌም፤ የኢየሩሳሌምን ጥፋት አታሳየን” ሊሉ አይችሉም፡፡

በሁለተኛ ደረጃ የበቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን፣ ዶግማዋንና ቀኖናዋን በግል ምልከታቸው በሥጋዊ ድካማቸው ደረጃ ዝቅ አድርገው “ምን አለበት፣ ምን ችግር አለው፣ ብዙ ባናካብድ” በሚሉ ሰበቦች ታስረው ቤተ ክርስቲያንን ያወቁ የሚመስላቸው ነገር ግን ያላወቁ ወጣቶች ናቸው፡፡ ለእነዚህ ዓይነቶቹ ምእመናን ቤተ ክርስቲያን የምታስፈልጋቸው ሥጋዊ ፈተናዎች (ሥራ ማጣት፣ ከወዳጃቸው ጋር መጋጨት፣ ሥጋዊ ደዌ፣ የኑሮ መክበድ፣ የትምህርት ጉዳይ፣ …) ሲያስጨንቃቸው ብቻ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን የሰማያዊና የዘለዓለማዊ ሕይወት ሰጪነት፣ የቤተ ክርስቲያን የነፍስ መጋቢነት አይታያቸውም፡፡

ሩጫቸው ምድራዊ ስኬት እስከ ማግኘትና መጎናጸፍ ድረስ ብቻ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ አሳስቧቸው ሳይሆን ለአገልግሎት የሚመጡት ለሥጋዊ ዓላማ ብቻ ነውና ጥያቄአቸው መልስ ሲያገኝ (ሥራ ወይም ትዳር ሲይዙ፣ …) ከቤተ ክርስቲያንም ይኮበልላሉ፡፡

በሦስተኛ ደረጃ ቤተ ክርስቲያንን ባልተረጋገጠና በተምታታ መረጃ በአላዋቂዎች ትምህርት ተመርኩዘው እናውቃለን የሚሉት ናቸው፡፡ በዚህኛው የዕውቀት ደረጃ ብዙ ወጣት ምእመናን ቤተ ክርስቲያን ለዘመናዊነት፣ ሠርቶ ለመለወጥ፣ ራስን ለማሳደግ ጠላት አድረገው ይስሏታል፡፡ መንፈሳዊነትንና ለቤተ ክርስቲያን አሳቢነትን ራስን ካለመንከባከብ፣ ንጽሕናን ካለመጠበቅ እና ሥራና ትምህርትን እርግፍ አድርጎ ትቶ የብህትውና ኑሮ ከመኖር ጋር የሚያዛምዱ ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች በሕይወታቸው ውስጥ እግዚአብሔርን በፈራጅነቱ፣ በቀጪነቱ ፈርተው ያመልኩታል እንጂ ከፍቅር የመነጨ ፈሪሃ እግዚአብሔር አይኖራቸውም፡፡ የእንደዚህ ዓይነት ሰዎች ሌላው መለያ ባሕርያቸው በመንፈሳዊ መንገዳቸው ፊት ለፊት የሚታያቸው የክርስቶስ ሕይወት፣ አልያም የአበው ቅዱሳን ተጋድሎ አይደለም። ከዚያ ይልቅ በቅርብ የሚያገኙትን አገልጋይ የፍጹምነት ምሳሌ አድርገው ይስሉታል፡፡ እነዚህ ወጣቶች ከቤተ ክርስቲያን ይልቅ እነዚህን ሰዎች ከማምለክ ባልተናነሰ ሲያዳምጡ ይስተዋላል፡፡ በአጠቃላይ ሦስቱም ትክክለኛ መንገዶች አይደሉም፡፡

ይቆየን፡፡

ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት ፳፯ ዓመት ቁጥር ፪ ሰኔ ፳፻፲፩ ዓ.ም

የእመቤታችን ትንሣኤ እና ዕርገት

“በጊዜውም ያለ ጊዜውም ጽና” (፪ኛጢሞ. ፬፥፪)

በእንዳለ ደምስስ

ጊዜ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ከሰጣቸው በረከቶች አንዱ ነው፡፡ ቀኑንም በሴኮንድ፣ በደቂቃ፣ በሰዓት፣ ሰዓቱንም በቀን ለክቶና ሰፍሮ እንጠቀምበት ዘንድ ሰጥቶናል፡፡ ነገር ግን የተሰጠንን ጊዜ በአግባቡ የምንጠቀም ስንቶቻችን ነን? ሁሉንም ነገር ለማከናወን ጊዜ አስፈላጊ መሆኑን ጠቢቡ ሰሎሞን ሲገልጽም “ለሁሉ ጊዜ አለው፤ ከፀሐይ በታችም ስለሆነ ነገር ሁሉ ጊዜ አለው …” በማለት ጊዜ ለፍጥረታት ሁሉ አስፈላጊ መሆኑን ይነግረናል፡፡

የጊዜን አስፈላጊነት ከተረዳን ማንኛውም ነገር በጊዜ ውስጥ የተለካና የተወሰነ እንደመሆኑ መጠን በሰው አእምሮ ወይም ፍላጎት አሁን ይከናወን ዘንድ የምንፈልገው ነገር በእግዚአብሔር ዘንድ ግን ገና ከሆነ የእግዚአብሔርን ጊዜ በጽናት መጠበቅ እንደሚያስፈልግ ሐዋርያው ይነግረናል፡፡ “በጊዜውም ያለ ጊዜውም ጽና” (፪ኛጢሞ. ፬፥፪) በማለት፡፡የእግዚአብሔርን ጊዜ መጠበቅ ደግሞ ዋጋ ያሰጣልና በጊዜውም ያለ ጊዜውም መጽናት ይገባል፡፡

እግዚአብሔር ጊዜን ለክቶ እንደሰጠን ሁሉ የሚያስፈልገንን ሁሉ ይሰጠን ዘንድም ጊዜ አለው፡፡ ነገር ግን የሰው ልጆች ደግሞ በተቃራኒው የምንሻውን ነገር ለማግኘት እንቸኩላለን፤ ሁሉንም ነገር አሁን ካልተደረገልን ብለን ከእግዚአብሔር ጋር ክርክር የምንገጥም፣ ባይደረግልን ደግሞ ከአምላካችን ጋር ለመጣላት የምንሞክር ብዙዎች ነን፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ላይ ከማጉረምረም ይልቅ ያላደረገልን ከእኛ አንድ ነገር የጎደለ ነገር እንዳለ በመረዳት በጸሎት በመትጋት የምንሻውን ነገር እስኪሰጠን ድረስ በትዕግሥት እግዚአብሔርን ደጅ መጽናት ያስፈልጋል፡፡

ለእኛ ጊዜው ነው፤ አሁን ሊሰጠን ወይም ሊያደርግልን ይገባል ብለን እንደምንለምነው ሁሉ እግዚአብሔር ፈቃዱ ሲሆን ባልታሰበ ጊዜና ሁኔታ ውስጥም ወደ እኛ ሊቀርብና ሊያከናውንልን ይችላል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ጌርጌሴኖን መንደር በደረሰ ጊዜ ሁለት አጋንንት ያደሩባቸው ሰዎች ከመቃብር ቦታ ወጥተው አገኛቸው፡፡ ክፉዎች ናቸውና በዚያ መንገድ ማንም ደፍሮ ማለፍ እስከማይችል ድረስ በእነዚህ አጋንንት ባደረባቸው ሁለት ሰዎች ቁጥጥር ሥር የነበረ ቦታ ነው፡፡ ነገር ግን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እነርሱ ቀርቦ ባዩት ጊዜ እየራዱና እየተንቀጠቀጡ “የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ሆይ ከአንተ ጋር ምን አለን? ጊዜው ሳይደርስ ልታሠቃየን ወደዚህ መጣህን?” እያሉ አጋንንቱ ጮኹ፡፡ በአቅራቢያቸው ወደሚገኙት እሪያዎች ይሰዳቸው ዘንድ ተማጸኑት፡፡ ጌታችንም እንደ ልመናቸው ይሄዱ ዘንድ ሰደዳቸው፡፡ አጋንነቱም በእሪያዎቹ ላይ እያደሩ ወደ ባሕሩ ወደቁ፡፡ (ማቴ. ፰፥፳፰-፳፱) እግዚአብሔር በራሱ ጊዜ ሁሉ ይቻለዋልና እንዲህም ያደርጋል፡፡

እኛ ያስፈልጉናል የምንላቸው ነገሮች ከእግዚአብሔር የሚለዩን፣ በሕይወታችን ውስጥ ትልቁን ጠባሳ ትተው የሚያልፉ ሆነው ሊገኙ ይችላሉና ስለምንለምነው ነገር ሁሉ በጸሎት የታገዘ ሕይወት ሊኖረን ይገባል፡፡ የምንሻው ነገር ሳይፈጸም ቢዘገይ የእግዚአብሔር ፈቃዱ አይደለምና ጊዜው ሲደርስ ያከናውንልን ዘንድ መጽናት ከእኛ ይጠበቃል፡፡ የምንሻውን መጠየቅ ብቻ ሳይሆን ለሕይወታችን እንደሚያስፈልግና እንደማያስፈልግ መለየት ከእኛ ይጠበቃል፡፡ የምንጠይቀው ነገር ከእግዚአብሔር ሊለየን፣ ከአምልኮት ሊያርቀን ይችላልና ስለምንጠይቀው ነገር ጥንቃቄ ልናደረግ ይገባል፡፡ እንደ ዘብድዎስ ልጆች ማለትም የዮሐንስ እና የያዕቆብ እናት “የምትለምኑትን አታውቁም” እስክንባል ራሳችንን ለተግሣጽ አሳልፈን እንዳንሰጥ ትዕግሥትን ገንዘብ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

የዮሐንስ እና የያዕቆብ እናት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አንድ ጥያቄ ጠይቃዋለች፡፡ በሰው ሰውኛው አስተሳሳብ በዚህ ዓለም ላይ ሊነግሥ የመጣ መስሏታልና በመንግሥቱ አንዱን ልጇን በቀኛዝማችነት በቀኙ፣ ሁለተኛውንም ልጇን በግራዝማችነት በግራው በጋሻ ጃግሬነት እንዲያቆምላት ጠየቀችው፡፡ “እነዚህን ሁለቱን ልጆቼን በመንግሥትህ አንዱን በቀኝህ፣ አንዱንም በግራህ እንዲቀመጡ አድርግልኝ” አለችው፡፡ እርሱም “የምትለምኑትን አታውቁም፣ እኔ የምጠጣውን ጽዋ መጠጣት፣ ትችላላችሁን? …” ሲል ገስጿታል፡፡ ይህ ታሪክ ከሚያስፈልገን ነገር ውጪ ለእኛ ስለመሰለን ብቻ መጠየቅ እንደማይገባን ትልቅ ማሳያ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሕይወትን የለመንን መስሎን ሞትን እንደነ ዮሐንስ እናት የምለምን እንኖራለን፡፡

እግዚአብሔር ሁሉንም በጊዜው የሚያከናውን አምላክ ነው፡፡ የምንለምነውን ባለማወቃችን፣ የራሳችንን ፍላጎት ብቻ በማስቀደማችን ከእግዚአብሔር አንድነት እንለያለን፡፡ “ለምንድነው እኔ በሚያስፈልገኝ ጊዜ እና ሰዓት የማያከናውንልኝ? እኔ አሁን ነው የምፈልገው!” እያልን ከእግዚአብሔር ጋር ሙግት የምንገጥም ብዙዎች ነን፡፡ ነገር ግን በጊዜውም ያለ ጊዜውም በመጽናት የእግዚአብሔርን ጊዜ መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ በራሳችን ፈቃድ ብቻ ተመሥርተን የምናከናውናቸው ተግባራት ሁሉ ለውድቀት የሚዳርጉን ናቸውና፡፡

ለመሆኑ የእግዚአብሔር ጊዜ መቼ ነው? እግዚአብሔር እያንዳንዱን ነገር ሲያከናውን በዕቅድ ነው፡፡ እግዚአብሔር እንደ ሰው አይደለም አይቸኩልም፣ አይዘገይምም፡፡ ዘግይቶ ወይም ቸኩሎ የፈጠረው አንዳች ነገር የለም፡፡ ሁሉንም በጊዜው ውብ አድርጎ ሠርቶታልና የሠራውም ሁሉ መልካም ነው፡፡ “ነገርን ሁሉ በጊዜው ውብ አድርጎ ሠራው” (መክ. ፫፥፲፩) እንዲል፡፡ በዕቅድና ሁሉን በጊዜው ባያከናውን ኖሮ በስድስቱ ቀናት እያንዳንዱን ፍጥረት ባልፈጠረ ነበር፡፡ ስለዚህ ከሰው ልጆች የሚፈለገው የእግዚእሔርን ጊዜ በትዕግሥት መጠበቅ ነው፡፡ “ … ቢዘገይም በእርግጥ ይመጣልና ታገሠው፤ እርሱ አይዘገይም” (ዕንባ. ፪፥፫) እንደተባለ፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ሰዎች በላከው መልእክቱ “በበጎ ምግባር ጸንተው ለሚታገሡ ምስጋናና ክብርን፣ የማይጠፋ ሕይወትንም ለሚሹ እርሱ ለዘለዓለም ሕይወትን ይሰጣቸዋል” (ሮሜ. ፪፥፯) በማለት እንደገለጸው ለእግዚአብሔር የምንመች፣ እንደ ቃሉም የምንመላለስ ሆነን በመገኘት በጾምና በጸሎት በመትጋት እግዚአብሔር ሊያከናውንልን የምንሻውን ነገር በትዕግሥት ደጅ በመጥናት መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ብቻ አያበቃም ለዕብራውያን ሰዎች በላከው መልእክቱም “ነገር ግን የእግዚአብሔርን ፈቃድ አድርጋችሁ የተሰጣችሁን ተስፋ ታገኙ ዘንድ መታገሥ ያስፈልጋችኋል” ሲል በመታገሥና በጽናት በሃይማኖት ቀንቶ፣ በምግባር ታንጾ መኖር ከሰው ልጆች ሁሉ ይፈለጋል፡፡ እግዚአብሔር እያንዳንዳችን የምንሻውን ብቻ ሳይሆን እርሱ ያዘጋጀልንን ሁሉ ይሰጠን ዘንድ ፈቃዱ ነውና በጊዜውም ያለ ጊዜውም ጸንተን እንቁም፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጉባኤ-ቃና መጽሔት-ነሐሴ-2016-ዓ.ም

ጉባኤ-ቃና መጽሔት-ነሐሴ-2016-ዓ.ም

ጽንሰታ ለማርያም

ጽንሰታ ለማርያም

ነሐሴ ፯ ቀን እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤልን ወደ ከበረና ከፍ ከፍ ወዳለ ጻድቅ ኢያቄም ላከው፡፡ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ፅንሰቷንና ልደቷን በእርሱም ለዓለሙ ሁሉ ድኅነትና ተድላ ደስታ እንደሚሆን ነገረው፡፡

ይህ ጻድቅ ሰው ኢያቄምና የከበረች ሚስቱ ሐና ልጅ ሳይወልዱ ሸመገሉ፡፡ የከበረች ሐና መካን ሁናለችና ስለዚህም እጅግ ያዝኑ ነበር፤ የእስራኤል ልጆች ልጅ ያልወለደውን ከእግዚአብሔር በረከትን ያጣ ነው እያሉ ያቀልሉት ነበርና፡፡ እነርሱም ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ዘወትር ፈጽሞ ይለምኑ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ ወንድ ልጅን ወይም ሴት ልጅን ቢወልዱ ለእግዚአብሔር ቤት አገልጋይ ሊያደርጉት ስዕለትን ተሳሉ፡፡ የልቡናቸውን መሻት የሆነውን ልጅ እንዲሰጣቸው እግዚአብሔርን ዘወትር በቤተ መቅደስ ተገኝተው ዕንባቸውን እያፈሰሱ መማጸናቸውን አላቋረጡም፡፡

ከዕለታት በአንድ ቀንም የከበረ ኢያቄምም በተራራ ላይ ሳለ ሲጸልይና ሲማልድ እነሆ እንቅልፍ እንቅልፍ ብሎት ተኛ፡፡ ያን ጊዜ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ተገለጸለት፡፡ እንዲህም አለው፡- “ሚስትህ ሐና ትፀንሳለች ዓለም ሁሉ ደስ የሚሰኝባትን የብዙዎችም ዐይነ ልቡናቸው በእርሷ የሚበራላቸውን በእርሷም ድኅነት የሚሆንባትን ሴት ልጅን ትወልድልሃለች” አለው፡፡

ሐናም በበኩሏ “አቤቱ ጌታዬ የአባቶቼ የእስራኤል አምላክ እኔ ባርያህ እለምንሃለሁ፤ ስማኝ ለዓይኔ ማረፊያ ለልቤ ተስፋ የምትሆነኝ የተባረከች ሴት ልጅ የማኅፀኔን ፍሬ ስጠኝ” ብላ ስትለምን ዋለች፡፡ ርግብ ከልጆቿ ጋር ስትጫወት ዓይታም በተሰበረ ልብ ውስጥ ሆና “አቤቱ ጌታዬ ለዚች ግእዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሳኸኝ?” ብላ ምርር ብላ አለቀሰች፡፡

ሐና እና ኢያቄም ከካህኑ ዘካርያስ ዘንድ ሄደው “አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሔርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን፤ ሴት ልጅም ብንወልድ ማይ(ውኃ) ቀድታ፣ መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ፣ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን” ብለው ስዕለት ገቡ፡፡ ካህኑ ዘካርያስም “እግዚአብሔር ጸሎታችሁን ይስማችሁ፤ ስዕለታችሁን ይቀበልላችሁ፤ የልቡናችሁን መሻት ይፈጽምላችሁ” ብሎ ቡራኬ ሰጥቶ ሸኛቸው።

ሐና እና ኢያቄም ዕለቱን ራእይ ዓይተው አደሩ፡፡ ራእዩም እንዴት ነው ቢሉ፡- ኢያቄም ፯ቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ርግብ ወርዳ በሐና ራስ ላይ ስታርፍ፤ በጆሮዋም ገብታ በማኅፀኗ ስትተኛ አየ፡፡ ሐናም የኢያቄም መቋሚያ ለምልማ አፍርታ ፍጥረት ሁሉ ሲመገባት አየች፡፡ ከዚህም በኋላ ኢያቄም ያየውን ራእይ ለሐና፣ ሐና ያየችውን ራእይ ደግሞ ለኢያቄም በመንገር ራሳቸውን እግዚአብሔር ለገለጸላቸው ነገር ለማዘጋጀት ተስማሙ፡፡

ሁለቱም በአንድ ልብ ሆነው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም፤ ፈቃደ እግዚአብሔር ቢሆን ነው ብለው “አዳምንና ሔዋንን ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት ብሎ ያበሰረ አምላክ ለኛስ ይልክልን የለምን?” ብለው ዕለቱን መኝታ ለይተው እስከ ፯ ቀን ድረስ ሰነበቱ፡፡ ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ “ከሰው የበለጠች፤ ከመላእክት የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላችሁ” ብሎ ለሐና ነገራት፡፡

በፈቃደ እግዚአብሔር፣ በብሥራተ መልአክ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም ነሐሴ ፯ ቀን ተፀነሰች፡:

ቅዱስ ያሬድ “ማርያምሰ ተኀቱ እምትካት ውስተ ከርሱ ለአዳም ከመ ባሕርይ ጸዓዳ፤ ማርያምስ ከጥንት ጀምሮ በአዳም ባሕርይ ውስጥ እንደ ነጭ ዕንቁ ታበራለች” በማለት እንደተናገረው እግዚአብሔር ቅድስት ድንግል ማርያምን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ድኅነት መሠረት እንዳደረጋት፣ ሊመረመር በማይችል ጥበቡም እንዳዘጋጃት ተናግሯል፡፡ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ “ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤   በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ” ብሎ አመስግኗታል፡፡

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን መሠረት አድርጋ ዕለቱን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምልጃዋ በረከቷ በሁላችን ላይ ይደር፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡ ስንክሳር ነሐሴ  ቀን

“ሞት በጥር፤በነሐሴ መቃብር”

ሞት በጥር፤ በነሐሴ መቃብር”

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩ ቀን ፵፱ ዓ.ም ከዚህ ዓለም ድካም ማረፏን ነገረ ማርያም ያስረዳል፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ማረፍን የተመለከቱት ቅዱሳን ሐዋርያትም ሊቀብሯት ወደ ጌቴሴማኒ ይዘዋት ሲሔዱ አይሁድ “እንደ ልጇ ተነሣች፤ ዐረገች እያሉ እንዳያውኩን በእሳት እናቃጥላት” ብለው በክፋት ተነሣሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም አጎበሩን ይዞ ሊያወርዳት ሲል የእግዚአብሔር መልአክ ሁለት እጆቹን ቀሰፈው፡፡ የአይሁድን ክፋት የተመለከተው አምላካችን ቅዱስ እግዚአብሔር እመቤታችንን ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን አስከትሎ በደመና ነጥቆ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያትም እመቤታችን ያለችበት ቦታ እንዲገለጥላቸው ባረፈች በስምንተኛው ወር ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ ገብተው እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቅ ጀመሩ፡፡ ከዚህ ላይ “ስምንት ወር ሙሉ ምን ይዘው ቆይተው ነሐሴ ላይ ሱባዔ ገቡ?” የሚል ጥያቄ ሊነሣ ይችላል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ከስብከተ ወንጌል፣ ከጾም፣ ከጸሎት፣ ከገቢረ ተአምራት፣ ተለይተው እንደማያውቁ መንፈሳዊ ሕይወታቸው ምስክር ነው፡፡

ከፊታቸው የዐቢይ ጾም፣ ከዚያም በዓለ ሃምሳ፣ ቀጥሎም የአገልግሎታቸው መጀመሪያ የሆነው የሐዋርያት ጾም ስለሚከተል ከሰው ተለይተው ሱባዔ ገብተው ጾም ጸሎት የጀመሩት ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምሮ ነው፡፡ ለሁለት ሱባኤ በጾም ጸሎት ከቆዩ በኋላ እግዚአብሔር ጸሎታቸውን ሰምቶ ነሐሴ ፲፬ ቀን የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው በክብር ገንዘው በጌቴሴማኒ ቀብረዋታል፡፡ እሷም እንደ ልጇ እንደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ትንሣኤ” ያሰኘውም ይህ ታሪክ ነው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ሲሰብክ ቆይቶ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ወደ ሰማይ ስታርግ አገኛት፡፡ በዚህ ጊዜ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?” ብሎ ትንሣኤዋን ባለማየቱ ኀዘን ስለ ተሰማው ከደመናው ወደ መሬት ይወድቅ ዘንድ ወደደ፡፡ እመቤታችንም “አይዞህ አትዘን፤ ባልንጀሮችህ ሐዋርያት ያላዩትን ትንሣኤዬን አንተ አይተሃል” ብላ ከሙታን ተለይታ መነሣቷንና ማረጓን እንዲነግራቸው ካዘዘችው በኋላ የተገነዘችበትን ሰበን ሰጠችው፡፡

ሐዋርያው ቶማስም ትእዛዟን ተቀብሎ ወደ ሐዋርያት በመሄድ ምንም እንዳልሰማ እንዳላየ መስሎ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” ሲል ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይሆናል?” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ በፊት የክርስቶስን ትንሣኤ መጠራጠሩን ጠቅሶ እየገሠፀ ስለ እመቤታችን መቀበር እነርሱ የሚነግሩትን ሁሉ መቀበል እንደሚገባው ለቅዱስ ቶማስ አስረዳው፡፡ በዚህ ብቻ ሳያበቃም ሐዋርያት የቅዱስ ቶማስን ጥርጣሬ ለማስወገድ ሲሉ የእመቤታችንን ክቡር ሥጋ ለቅዱስ ቶማስ ለማሳየት ወደ መቃብሯ ጌቴሴማኒ ሄደው መቃብሯን ቢከፍቱት የእመቤታችንን ሥጋ ማግኘት አልቻሉም፡፡

ቅዱስ ቶማስም “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ እንደ ልጇ ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ስታርግ አግኝቻታለሁ” ብሎ የሰጠችውን ሰበን ለሐዋርያት ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት እየተደሰቱ ሰበኑን ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ በቅዳሴ ጊዜ ሠራዒ ዲያቆኑ በሚይዘው መስቀል ላይ የሚታሠረው መቀነት መሰል ልብስ፤ እንዲሁም አባቶች ካህናት በእጅ መስቀላቸው ላይ የሚያስሩት ቀጭን ልብስና በራሳቸው የሚጠመጥሙት ነጭ ሻሽ የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡

በዓመቱ ቅዱሳን ሐዋርያት “ቶማስ የእመቤታችን ትንሣኤዋንና ዕርገቷን አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን?” ብለው ከየሀገረ ስብከታቸው ተሰባስበው ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ በመያዝ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሥጋ እንዲሰጣቸው እግዚአብሔርን ተማጸኑ፡፡ ጌታችንም ልመናቸውን ተቀብሎ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችንን መንበር፤ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፤ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ እመቤታችንንም ሐዋርያትንም አቍርቧቸዋል፡፡ እነርሱም እመቤታችንን በዓይናቸው ከማየት ባሻገር አብረው ሥጋውን ደሙን ተቀብለዋል (ትርጓሜ ውዳሴ ማርያም)፡፡

ይህንን ትምህርት መሠረት በማድረግ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ከነሐሴ ፩-፲፬ ያለውን ሁለት ሱባዔ ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ ሆኖ በምእመናን ዘንድ መጾም እንደሚገባው ሥርዓት ሠርተውልናል (ፍት.ነገ.አን. ፲፭)፡፡ ይህ ጾምም “ጾመ ማርያም”  ወይም “ጾመ ፍልሰታ ለማርያም” እየተባለ ይጠራል፡፡ “ፍልሰት” የሚለው ቃልም “ፈለሰ ሔደ፤ ተሰደደ” ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጕሙም ከአንድ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር መሔድን ያመለክታል፡፡ “ፍልሰታ ለማርያም” ሲልም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ካረፈች በኋላ ከጌቴሴማኒ ወደ ገነት መወሰዷን የሚያስረዳ ነው፡፡

በጾመ ፍልሰታ በቤተ ክርስቲያናችን በየቀኑ በማሕሌቱ፣ በሰዓታቱና በቅዳሴው በሚደርሰው ቃለ እግዚአብሔር ነገረ ማርያም ማለትም የእመቤታችን ከመፀነሷ ጀምሮ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለው ታሪኳ፣ ለአምላክ ማደሪያነት መመረጧ፣ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ክብሯ፣ ርኅርራኄዋ፣ ደግነቷ፣ አማላጅነቷ፣ ሰውን ወዳድነቷ በስፋት ይነገራል፡፡ እመቤታችንን ከሚያወድሱ ድርሳናት መካከልም በተለይ ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከነገረ ማርያም ጋር በማዛመድ የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም፤ እንደዚሁም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌ (ከነገረ ክርስቶስ) እና ከነገረ ማርያም ጋር በማመሥጠር የሚያትተው ውዳሴ ማርያምም በስፋት ይጸለያል፤ ይቀደሳል፤ ይተረጐማል፡፡ በሰንበታት የሚዘመሩ መዝሙራት፤ በየዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለእናትነት  በእግዚአብሔር መመረጧን፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን፣ ክብሯን፣ ቅድስናዋን፣ ንጽሕናዋን የሚያወሱ ናቸው፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋና በረከት አይለየን፡፡

“የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራል፤ ያድናቸውማል”

(መዝ. ፴፬፥፯)

ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ ቀን ሕፃኑ ቂርቆስንና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ከሚነደው እቶን እሳት ያዳነበት ዕለት ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም በየዓመቱ ዕለቱን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡ የእነዚህም ቅዱሳን ታሪክ በስንክሳር እንዲህ ይተረካል፡፡

በዚህችም ቀን ሕፃኑ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራን ተቀበሉ፡፡ ይህም ሕፃን ዕደሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር እናቱ ይዛው ሸሸች፤ በዚያም የሸሸችውን መኮንን አገኘችው፡፡

ሰዎችም ነገር ሠሩባት፤ ወደ አርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት፤ እርሷም “መኰንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ፤ አማልእክቶችህ ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ” አለችው፡፡

ሕፃኑም አለበት ጭፍራውን ልኮ ወደርሱ አስመጣው፤ ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና “አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ?” አለው፡፡ ሕፃኑም መልሶ “አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል፤ ለአንተ ግን ኃዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው፡፡ መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም፤ ብሏልና” አለው፡፡ እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ፡፡ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን፣ መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው፤ ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ፡፡

መኰንኑም በአፈረ ጊዜ በየዓይነቱ በሆነ ስቃይ ታላላቆች የማይችሉትን ታላቅና አስጨናቂ የሆነ ስቃይን አሰቃየው፡፡ እናቱንም ከርሱ ጋር እንደ እርሱ አሰቃያት፤ እግዚአብሔርም ያለ ምንም ጉዳት ያስነሣቸው ነበር፡፡ ብዙዎች አሕዛብም ይህን ዐይተው አደነቁ፤ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ፤ የሰማዕትነትም አክሊል ተቀበሉ፡፡

በሕፃኑ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት፡፡ ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችንም አደረገ፤ ብዙዎች በሽተኛቹንም አዳናቸው፡፡ ከዚህም በኋላ መኰንኑ በታላቅ የናስ ጋን ውስጥ ውኃ ጨምረው በእሳት ያፈሉት ዘንድ አዘዘ፡፡ የፍላቱም ድምጽ እንደ ክረምት ነጐድጓድ ሆነ፤ ያን ጊዜም ፍርሃትና የሃይማኖት ጉድለት በእናቱ ላይ ደረሰባት፤ ሕፃኑም ስለ እናቱ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡

ያን ጊዜ ጌታችን ልቧን ወደ ሰማይ አሳርጎ ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁ የብርሃን ማደሪያዎችን አየች፤ ከዚህም በኋላ ጸናች፤ እግዚአብሔርንም አመሰገነችው፡፡ ልጅዋንም “ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ፤ እኔም ልጅህ ነኝ” አለችው፡፡ “ያቺ ከእኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት” አለች፡፡ ወደዚያ ወደ ጋኑ ውስጥ በገቡ ጊዜም የውኃው ፍልሐት እንደ ንጋት ጊዜ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡ ከእግዚአብሔር የታዘዘ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወርዶ የእሳቱን ኃይል አቀዝቅዞታልና፡፡

ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሥጋቸው ተቆራርጦ እስከሚወድቅ ድረስ በመቃጥን ውስጥ አድርገው እንዲጎትቷቸው አዘዘ፡፡ ከእግዚአብሔርም የታዘዘ መልአክ አዳናቸው፡፡ መኮንኑም በታላቅ ስቃይ ያሰቃያቸው ዘንድ አስቦ እስኪመክር ድረስ በወኅኒ ቤት ዘጋባቸው፡፡

ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው፣ አረጋጋውም፡፡ ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቂርቆስና በኢየሉጣ ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸውም ትድረሰን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡ ስንክሳር ዘወርኀ ሐምሌ ፲፱

ለቅዱሳን የተሰጠችን ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ እማልዳችኋለሁ” (ይሁ.፩፥፫)

“ለቅዱሳን የተሰጠችን ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ እማልዳችኋለሁ” (ይሁ.፩፥፫)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮዋን በመስበክ፣ የሚደርስባቸውን መከራ ሁሉ ታግሰው እስከ መጨረሻው በመጋደል ያሉትን በማጽናት፣ በእግዚአብሔር ቃል መረብነት አሕዛብንና አረማውያንን ካለማመን ወደ ማመን ይመጡ ዘንድ በማጥመድ ወደ ክርስያኖች ኅብረት የሚያስገቡትን ቅዱሳንን ቀን ሰይማ በዓላቸውን ታከብራለች፡፡ ከእነዚህ ቁጥር ስፍር ከሌላቸው ቅዱሳን ሰማዕታት መካከል ደግሞ የሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ እረፍት ሐምሌ ፭ ቀን በየዓመቱ በዓላቸውን በድምቀት ታከብራለች፡፡ የእነዚህ ቅዱሳን ሰማዕታት ሕይወት ምን ይመስል ነበር? እንዴትስ ተጠሩ? አገልግሎታቸውንና ተጋድሏቸው በተመለከተ ቀጥለን እናቀርባለን፡፡

ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ በገሊላ ባሕር ከወንደሙ እንድርያስ ጋር እንደ ልማዳቸው ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ሳሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወልጌል መረብነት ሰዎችን ወደ ክርስትና በማምጣት ያጠምዱ ዘንድ በቅድሚያ ቅዱስ ጴጥሮስን ቀጥሎም እንድርያስን ጠርቷቸዋል፡፡ “በገሊላ ባሕር ዳር ሲመላለስም ሁለቱን ወንድማማቾች ጴጥሮስ የተባለ ስምዖንና ወንድሙን እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ዓሣ አጥማጆችም ነበሩና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ‘ኑ ተከተሉኝ፤ ሰውን የምታጠምዱ እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ’ አላቸው፡፡ ወዲያውኑ መረባቸውን ትተው ተከተሉት” እንዲል (ማቴ. ፬፥፲፰-፳)

የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አመራረጥ ደግሞ በተአምራት ነው፡፡ ጳውሎስ የተባለው ሳውል ለአይሁድ እምነት ታማኝና ይህንንም የሚቃወሙትን በማሳደድ የሚታወቅ የክርስትና ጠላት የነበረ ሰው ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ከድቅድቅ የኃጢአት ባሕር ውስጥ ሰዎችን ማውጣት ይቻለዋልና ሳውል ክርስቲያኖችን ይገድል፣ ያሳድድ ዘንድ በተሰማራበት ጠራው፡፡ “ሳውል ግን ገና አብያተ ቤተ ክርስቲያናትን ይቃወም ነበር፡፡ የሰውንም ቤት ሁሉ ይበረብር ነበር፤ ወንዶችና ሴቶችንም እየጎተተ ወደ ወኅኒ ቤት ያስገባቸው ነበር” በማለት እንደተገለጸው (ሐዋ. ፰፥፫) በዚህ ብቻ ሳይበቃው ሐዋርያትንም ያሳድድና ይገድል ዘንድ ከሊቀ ካህናቱ ዘንድ የፈቃድ ደብዳቤ ይሰጠው ዘንድ እስከመጠየቅ የደረሰ አሳዳጅ ነበር፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ይህንን ሲገልጽ “ሳውል ግን የጌታን ደቀ መዛሙርት ለመግደል ገና እየዛተ ወደ ሊቀ ካህናቱ ሄደ፡፡ ምን አልባት በመንገድ የሚያገኘው ሰው ቢኖር ወንዶችንም ሴቶችንም እያሰረ ወደ ኢየሩሳሌም ያመጣቸው ዘንድ በደማስቆ ላሉት ምኩራቦች የሥልጣን ደብዳቤ ከሊቀ ካህናቱ ለመነ፡፡” (ሐዋ. ፱፥፩-፪)

ሳውል ለሃይማኖቱ ቀናተኛ ነውና የሚሠራው ሁሉ ከእግዚአብሔር የሚለይ የኃጢአት ሥራ መሆኑን አልተረዳም፡፡ ቀዳሜ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ በአይሁድ እጅ ሲወገር የገዳዮቹንም ልብስ ጠባቂ የነበረ አሳዳጅ ነበር፡፡ (የሐዋ. ፯፥፶፰-፷) ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል፣ በወኅኒ ማጎር የዘወትር ሥራው አድርጓልና በዚህም ይደሰት ነበር፡፡ ነገር ግን ወደ ደማስቆ ሲሄድ ድንገት መብረቅ ከሰማይ ብልጭ አለበት፡፡ መቋቋም አልቻለምና በምድር ላይ ወደቀ፡፡ ወዲያውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚለውን ቃል ሰማ፡፡ ሳውልም የሰማውን ድምጽ መቋቋም እየተሳነው በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ “አንተ ማነህ?” ሲል ጠየቀ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፤ በሾተል ብረት ላይ ብትቆም ለአንተ ይብስብሃል” አለው፡፡ ሳውልም ምን እንዲያደርግ እንደሚፈልግ ጌታችንን በጠየቀው ጊዜ ወደ ከተማ እንዲገባና ሊያደርገው የሚገባውን በከተማው እንደሚነግሩት አስረዳው፡፡ ነገር ግን ሳውል ከወደቀበት ሲነሣ ዓይኖቹ ታውረው ስለነበር ማየት አልቻለም፡፡ እየመሩም ወደ ደማስቆ ወሰዱት ሳይበላና ሳይጠጣ ለሦስት ቀናት ቆየ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐናንያ ለተባለው ደቀ መዝሙር ተገልጦም ሳውልን ይፈውሰው ዘንድ ላከው፡፡ ሐናንያ የሳውልን ኃጢአት አንድ በአንድ እየዘረዘረ ከጌታችን ጋር ተከራክሯል፤ ነገር ግን ጌታችን ”ተነሥና ሂድ በአሕዛብና በነገሥታት በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ አድርጌዋለሁና፡፡ እኔም ስለ ስሜ መከራን ይቀበል ዘንድ እንዳለው አሳየዋለሁ” በማለት ነገረው፡፡ ሐናንያም ወደ ሳውል ሄዶ እጁን ጫነበት፤ ፈጥኖም ከዓይኖቹ እንደ ቅርፊት ያለ ነገር ወደቀ፤ ዐይኖቹም አዩ፤ ወዲያውም ተጠመቀ፡፡ ለሳምንታት በዚያ ከቆየም በኋላ በምኩራቦች እየተገኘ የጌታችን መድኃኒታችንን አምላክነት እየሰበከ ዞረ፡፡ አይሁድም ሳውልን ይገድሉት ዘንድ ተማከሩ፡፡ (ሐዋ.፱፥፩-፴፩)

ቅዱስ ጳውሎስም “የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ አይገባኝም” በማለት ራሱን በትኅትና ዝቅ በማድረግ ለወንጌል ታማኝ ሆኖ እስከ ሕይወቱ ፍጻሜ በተጋድሎ ኖሯል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ፲፬ መልእክታትን፣ ቅዱስ ጴጥሮስ ደግፖ ሁለት መልእክታትን በመጻፍም ብዙዎችን ከጣዖት አምልኮ፣ ከአሕዛብነትና ከአረማዊነት መልሶ ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስ የዮና ልጅ ስምዖን ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ (ዮሐ.፳፩፥፲፭) ነገር ግን ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን “እናንተስ ማን ትሉታላችሁ” ብሎ ሲጠይቃቸው ሐዋርያው ተነሣና፡- “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም ጌታችን “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህ፡፡ እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚችም አለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሏትም” በማለት ጴጥሮስ ብሎ ሰየመው፡፡ (ማቴ.፲፮፥፲፯—፲፰)
ጳውሎስን ደግሞ ጌታችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲጠራው በመጀመሪያ ስሙ ሳውል ብሎ ጠራው፤ በምስክርነቱ ጊዜ ደግሞ “ጳውሎስ ሆይ፥ በኢየሩሳሌም ስለ እኔ እንደ መሰከርህ እንዲሁ በሮሜም ትመሰክርልኝ ዘንድ ይገባሃልና፥ አይዞህ አለው፡፡” (የሐዋ.፳፫፥፲፩)
የቅዱስ ጴጥሮስ አገልግሎቱ በአብዛኛው ሕግ ለተጻፈላቸው፣ ነቢያት ለተላኩላቸው፣ መሥዋዕት ለሚያቀርቡ፣ ግርዛት ለተሰጣቸው ለአይሁድ ነበር፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የቅዱስ ጳውሎስ አገልግሎት የነበረው በአሕዛብ መካከል ነበር፡፡
በአገልግሎታቸውም ድንቅ ተአምራትን ፈጽመዋል፡፡ ለምሳሌ ስለ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፡፡ “እግዚአብሔርም በጳውሎስ እጅ የሚያስገርም ተአምራት ያደርግ ነበር፤ ስለዚህም ከአካሉ ጨርቅ ወይም ልብስ ወደ ድውዮች ይወስዱ ነበር፥ ደዌያቸውም ይለቃቸው ነበር ክፉዎች መናፍስትም ይወጡ ነበር፡፡” (የሐዋ.፲፱፥፲፩-፲፪) በኢዮጴም ጣቢታ የምትባል አገልጋይን ከሞተች፤ አጥበውም በሰገነት ከአኖሯት በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ካለበት ተጠርቶ ከጸለየ በኋላ ጣቢታ ሆይ ተነሽ ሲላት ዐይኖቿን እንደከፈተች ተጽፏል፡፡ (የሐዋ.፱፥፴፮—፵፪) በተመሳሳይ ቅዱስ ጳውሎስ አውጤኪስ የሚባል ከሦስተኛ ደርብ ወደ ታች ወድቆ የሞተን ጎልማሳ እንዲነሣ አድርጓል፡፡ (የሐዋ.፳፥፯—፲፪)
ሁለቱም ቅዱሳን ሐዋርያት በሮማው ቄሳር ኔሮን ዘመን ፷፯ ዓ.ም. ሰማዕትነትን ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ቁልቁል ተሰቅሎ ሰማዕትነት የተቀበለ ሲሆን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ አንገቱን ተቀልቶ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡
በረከታቸው ይደርብን፡፡

“እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን” (ዮሐ. ፳፥፳፮-፳፱)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሞቱ ሞትን ሽሮ በትንሣኤው ትንሣኤአችንን ካወጀልን በኋላ በሳምንቱ ሐዋርያት በዝግ ቤት ውስጥ ሆነው ሳሉ መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል እንደ ተነሣ እንዲሁ በር ክፍቱልኝ ሳይል በዝግ ቤት ውስጥ ሳሉ በመካከላቸው ተገኝቷል፡፡ ይህንንም ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያችን “ዳግም ትንሣኤ” በማለት በድምቀት ታከብረዋለች፡፡ ዳግም ትንሣኤ የተባለበት ምክንያትም በአከባበር፥ በሥርዓት የመጀመሪያውን ትንሣኤ ስለሚመስል ነው፡፡ የትንሣኤ ዕለት የሚባለው ቃለ እግዚአብሔር ሳይለወጥ፤ በሙሉ በዚህ ቀን ይደገማል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ “ሰላም ለሁላችሁ ይሁን!” በማለት ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት “ጌታችን አየነው” በማለት በደስታ ሲነግሩት እርሱ ግን “የችካሩን ምልክት ካላየሁ፣ ጣቴንም ወደ ተቸነከረበት ካልጨመርሁ፣ እጄንም ወደ ጎኑ ካላስገባሁ አላምንም” አላቸው፡፡ ቶማስ ትንሣኤ ሙታንን ከማያምኑ ከሰዱቃውያን ወገን በመሆኑ ለጥርጥር እንደዳረገው ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ዲዲሞስ የተባለው ቶማስ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡  “በኋላ እናንተ ‘አየን’ ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግን ‘ሰምቼአለሁ’ ብዬ  

ልመሰክር፤ ላስተምር? አይሆንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም” አለ፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፬-፳፮)

ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ የሐዋርያው ቶማስን ጥርጥር ለማስወገድ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት (ሐዋርያው ቶማስ ባለበት) በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ “ሰላም ለሁላችሁ ይሁን!”

በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡ ቶማስንም “ጣትህን ወዲህ አምጣ እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣ ወደ ጎኔ አግባ፤ እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን” ብሎ አሳየው፡፡ ቶማስም ጣቱን ወደ ተቸነከሩት እጆቹ፣ እጁንም ወደ ተወጋው ጎኑ ሲጨምር እርር ኩምትር አሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ “ጌታዬ አምላኬም” ብሎ አመነ፡፡ በዚህም ምክንያት የሳምንቱ ዕለተ ሰንበት የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመሆኑ “ዳግም ትንሣኤ” ተብሎ ይጠራል፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡