የማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን አጠቃቀም

መ/ር በትረ ማርያም

ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን እውነተኛና ሐሰተኛ መረጃዎችን በጽሑፍ፣ በድምጽ፣ በምስል ወድምጽና በመሳሰሉት መንገዶች ለሕዝብ የሚሰራጭበት የመገናኛ ዘዴ ነው። ሆኖም አንድ ሰው ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ሲጠቀም በሐሰቱ እንዳይጎዳ፣ በእውነቱ እንዲጠቀም እውነቱን ከሐሰት የሚለይበት ማንጸሪያ ወይም መመዘኛ ሊኖረው ያስፈልጋል፡፡ የተጻፈ ወይም የተነገረና የታየ ሁሉ እውነት አይደለምና።

የሰው ልጅ ለተለያየ ዓላማ አንድን ሐሳብ በፈለገው መንገድ ሊገልጽ ይችላል፡፡ ነገር ግን የገለጸበት መንገድና ሁኔታ ምን ዓይነት መረጃ፣ ለማን፣ እንዴት፣ ወዘተ ለሚሉት ጥያቄዎች በተገቢው መንገድ ምላሽ የሚሰጥ መሆን ይገባዋል፡፡ መረጃውም ሊጠቅምና ሊጎዳ እንደሚችል በቅድሚያ መረዳት ይገባል፡፡ እውነትን ቢናገር እንኳ የተናገረው ምን አስቦ ወይም ለምን ዓላማ እንደሆነ ስለማናውቅ የመታለል ዕድላችን ከፍ ያለ ሊሆን ይችላል።

ስለዚህ በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የሚለቀቁ መረጃዎች ትክክለኛ ከሆኑ አዎንታዊ ተጽእኖ በሐሰት የተሞሉ ከሆኑ ደግሞ አሉታዊ ተጽእኖ በማኅበረሰቡ ላይ የማሳደር አቅማቸው ከፍተኛ ነው፡፡ በዚህም መሠረት በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የተጻፉ ጽሑፎችን፣ የተለጠፉ የምስል ወድምጽ መልእክቶችን ስናይ ስለ ማንነታቸውና ስለ ውጤታቸው አዎንታዊነትና አሉታዊነት ለመረዳት መጠየቅ ያለብን ጥያቄዎች አሉ። ጥቂቶቹን ብንመለከት፡-

 . መልእክቱ ምንድን ነው?፡- በማኅበራዊ የመገናኛ ብዙኃን የተላለፈው ጉዳይ መልእክት ምንነት እና ፍሬ ነገር ምንድን ነው? የሚለውን መጠየቅ ያስፈልጋል። ዝም ብለን የጉዳዩን ምንነት ሳንረዳ ሌሎች ስላራገቡት የምንቀበለው መሆን የለበትም። በተአምረ ኢየሱስ የተጻፈ አንድ ታሪክ አለ።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛ አብነት ለመሆን ትምህርት ይማር ዘንድ ወደ መምህር ሄደ። (አስተውል ለመምህሩ ዕውቀትን የሰጠ ጌታ ለእኛ አብነት ለመሆን ሲል ሄደ እንጂ አዲስ ዕውቀት ለመገብየት አይደለም)። ከዚያ መምህሩ ፊደል ሊያስተምረው “አሌፍ” በል አለው። ጌታም “አሌፍ” አለ። ከአሌፍ ቀጥሎ ያለው ፊደል “ቤት” ነውና “ቤት” በል አለው።

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን መጀመሪያ የአሌፍ ትርጉሙ ምንድን ነው? የዚህን ምሥጢር ንገረኝና ቀጣዩን እለዋለሁ ብሎታል። ስለዚህ እኛም ጉዳዩን በቅርበት በስሜት ሕዋሳቶቻችን ዳስሰን፣ ዐይተንና ቀምሰን ያላረጋገጥነውን ጉዳይ ወይም በሃይማኖት ትምህርት ያልተማርነውን ጉዳይ የሆነ አካል ጽፎት ብናገኝ ስለተጻፈው ጽሑፍ ምንነት የጻፈውን አካል ጠይቀን ወይም በሌላ መንገድ መረዳት ይጠበቅብናል፡፡ ይህም የመልእክቱን ምንነት መለየትና መገንዘብ ያስችለናል፡፡

. ማን ጻፈው?፡- ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ “ይደልዎ ለዘያነብብ ቅድመ ይዝክር ስሞ ለበዓለ መጽሐፍ ወእምዝ ያንብብ ወይምሀር፤ የተጻፈን ነገር ለሚያነብ ሰው የተጻፈውን ጉዳይ ከማንበቡ በፊት የጸሓፊውን ማንነት ይወቅ፣ ካወቀ በኋላ አንብቦ ያነበበውን ያስተምር” ይላል። የጸሓፊውን ማንነት ማወቅ የጽሑፉን ስሜት እንድንረዳው ይረዳናል። ከዚያም ጽሑፉን አንብቦ የተጻፈበትን ዐውድ ተረድቶ ምን ለማለት እንደፈለገ በቀላሉ መረዳት ያስችላል፡፡ ክርስቶስን ሐዋርያት ብቻ ሳይሆኑ ብዙ ሰዎችም ተከትለውት ነበር። ነገር ግን የሚከተለው ሕዝብ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የነበረው አመለካከት የተለያየ ነበር። “መጥምቁ ዮሐንስ ነው የሚሉ አሉ፤ ሌሎችም ኤልያስ፣ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ፡፡”(ማቴ.፲፮፥፲፬)፡፡ አስተውል የሚከተሉትን ሰው ማንነት አለማወቅ ከትልቅ ክሕደት ውስጥ ይከታል። ፈጣሪያቸውን እንደ ፍጡር አቅርበውት ነበር። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ ቢላቸው ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” ብሎ ቢመልስ “አንተ ብፁዕ ነህ” ተብሎ ክብር ተሰጥቶታል።

በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ባለቤታቸው የማይታወቁ ብዙ ጽሑፎች እና የድምጽ እንዲሁም የምስል ወድምጽ መረጃዎች ይለቀቃሉ። በዚህን ጊዜ በአእምሯችን የሚጭኗቸው መልእክቶች ይኖሯቸዋል። ስለዚህ መልእክቱ ከእውነተኛነቱ አልፎ ክርስቲያናዊ ወይም ኦርቶዶክሳዊ ነው ወይ? የሚለውን መመዘን ያስፈልጋል። ስለዚህ ማኅበራዊ መገኛ ብዙኃን ስንጠቀም መምረጥ አለብን ማለት ነው።

. የት ተጻፈ?፡- ድርጊቱ የተፈጸመው የት ነው? የሚለው መታወቅ አለበት። በውጭ ሀገር የተደረገውን ድርጊት በሀገራችን እንደተደረገ እያደረጉ እያቀረቡ ሰውን ስሜታዊ የሚያደርጉ፣ ዋሽተው የሚያስዋሹ ብዙ ሰዎች አሉ። ስለዚህ የሆነን ድርጊት ወይም ጉዳይ አምነን ከመቀበላችን በፊት በተለያየ መንገድ ትክክለኛነቱን ማረጋገጥ ይገባል። ለማረጋገጥ በቂ ማስረጃ ካላገኘን ጉዳዩን ለሌሎች ከማካፈል መቆጠብ፣ እኛም ከመደናገጥና ከስሜታዊነት ርቀን በሰከነ መንገድ ልንጓዝ ያስፈልጋል፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ የሶስናን ታሪክ ሙሉውን ስናነብ የምናስተውለው አንድ ነገር አለ። ረበናት ከሶስና ጋር መተኛት ይፈልጋሉ። እርሷ ግን እምቢ ትላቸዋለች። በዚህ ምክንያት በሐሰት ይከሷታል። የሚመለከታቸው አካላትም ጉዳዩን ሳይመረምሩ ሶስናን ለመግደል ይዘጋጃሉ። ዳንኤል ግን ጉዳዩን እንመርምረው ብሎ የት አገኛችኋት ብሎ ሲጠይቃቸው ከተለያየ ቦታ ተናገሩ። በዚህ ጊዜ ውሸታቸው ታውቋል። ስለዚህ እኛም በውሸት እንዳንታለል “የት?” ብለን መጠየቅ አለብን።

. መቼ ተጻፈ? የሰማነው ወይም ያየነው ነገር መቼ የተፈጸመ ነው? የሚለውን ማወቅ ያስፈልጋል። ምክንያቱም ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ከዓመታት በፊት የተደረገውን ጉዳይ ዛሬ እንደተደረገ አድርገው ከዚህ ቀደም ያላየውን ሰው ያታልሉበታል። ከውጭ ሀገርም ይሁን በሀገር ውስጥ ከዓመታት በፊት የተቃጠለውን ቤት፣ የሞተውን ሰው ዛሬ የተደረገ አስመስለው ሰውን ከሰው ያጣሉበታል። ስለዚህ የምንሰማውን ነገር መቼ እንደተደረገ ማወቅ ያስፈልጋል። ጌታችን ሐዋርያትን በደብረ ዘይት ሰብስቦ ስለ ዳግም ምጽአት እና ምልክቶቹ ሲነግራቸው ይህ መቼ ይሆናል? ብለው ጠይቀውታል። (ማቴ. ፳፬፥፫) እኛም መረጃን ለማጣራት መቼ ብለን መጠየቅ አለብን። አለበለዚያ ግን ተሳስተን ልናሳስት የተሳሳተ መረጃ አጋርተን እኛንም ሌላውንም ልንጎዳበት እንችላለንና መጠንቀቅ አለብን።

. ስንት?፡- ብዙ ጊዜ አንዱ የሠራውን በደል ብዙ ሰው እንደሠራው አድርጎ ማቅረብ እና ብዙ ሰው የሠራውን አንድ ሰው ወይም ጥቂት ግለሰቦች እንደሠሩት አድርጎ መረጃ ሊለቀቅ ይችላል።

ለምሳሌ በአንዱ ሰው ወንጀል ያ ሰው የተወለደበትን ሰፈር ወይም ብሔር መስደብ ትልቅ ችግር ሊያስከትል የሚችል ነው። ተጠያቂም መሆን ካለበት ራሱ ተናጋሪው አካል ወይም ቡድን እንጂ በጅምላ የተወለዱበትን ቦታ መስደብ ትልቅ በደል ነው። ምናልባት ወንጀል ፈጻሚው ሰው በሥነ ምግባሩ ምክንያት ሕዝቡ የናቀው ሊሆን ይችላል። ስለዚህ አንድን ጉዳይ ዝም ብለን ከመቀበላችን በፊት ስንት ሰው አደረገው? የሚለውን መረጃ ጠይቀን ማወቅ ይጠበቅብናል ማለት ነው። ስንት የቦታን ስፋት፣ የጊዜን መጠን፣ የሰውን ብዛት ሊያሳውቀን ይችላልና። ብዙዎች የሠሩትን ወንጀል አንድ ሰው እንደሠራው አድርጎ ማቅረብም ሊኖር ይችላል።

፮. እንዴት?፡- በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የሚለቀቁ  አንዳንድ መልእክቶች ደግሞ ከነባራዊው እና ከተፈጥሯዊው ጉዳይ ያፈነገጡ ሊሆኑ ይችላሉ። ዝም ብለን የምንቀበላቸው አይደሉም። እኛ ከለመድነው እንዲሁም ከተማርነው እና ካየነው የተለየ ነገር ሲነገር እና ሲተላለፍ እንዴት? ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል።

፯. ለምን?፡- በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ብዙ መረጃዎች በተለያየ መንገድ ይለቀቃሉ። መልእክቶቹን የሚለቀው ሰው ግን ምክንያት አለው። እውነቱንም ይሁን ሐሰቱን መረጃው ለሚደርሳቸው አካላት ማሥረፅ የፈለገው ጉዳይ አለው። ስለዚህ አንድን መልእክት በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ተጽፎ ስናገኘው ቀጥታ በእኛ አረዳድ ብቻ ሳይሆን በጸሓፊው አረዳድ ልንረዳው ይገባል። መልእክቱን ዐይተን ቀጥታ ማመን የለብንም። ለምን ብለን መጠየቅ አለብን። አንድ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ በተማሪዎች የሚነገር ቀልድ (ተረት) አለ። በአንድ ወቅት ምሽት ላይ አንድ የተማሪዎች ማደሪያ ክፍል መቃጠል ይጀምራል። ከዚያ ተኝተው የነበሩ ተማሪዎች ይነቁና ማደሪያ ክፍላቸው እየተቃጠለ መሆኑን ሲያውቁ ራሳቸውን ለማትረፍ ተደናግጠው ራቁታቸውን እየሮጡ ይወጣሉ፡፡ ከዚያ ቤተ መጻሕፍት ቆይቶ የመጣ ተማሪ ወደ ቤቱ ሲመለስ ብዙ ሰው ራቁቱን እየሮጠ ያያል። ይህን ጊዜ እርሱም ልብሱን አውልቆ ተከተላቸው ይባላል። አሁን ይህ ሰው ያለ ምክንያት የሚንቀሳቀስ ሰው ነው። እነርሱስ ከምንቃጠል ብለው ለማምለጥ በደመ ነፍስ ያደረጉት ነው። እርሱ ግን ዝም ብሎ እነርሱን ብቻ ዐይቶ ምክንያቱን ሳይረዳ አውልቆ ተከትሏቸዋል። እኛም በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የሆነ ታወቂ ሰው ወይም የማኅበራዊ አንቂ(Activist) ግለሰብ ስለጻፈው እሱን ተከትለን የምናስተጋባና ለሌሎች የምናጋራ መሆን የለብንም።

ግለሰቡ ለሆነ ዓላማ ውሸቱንም ይሁን እውነቱን መረጃውን ሲያዘጋጀው የሚያስከትለውን ችግር ተረድቶም ሆን ሳይረዳ ወይም ሆነ ብሎም ሲያደርገው ተከፍሎት ሊሆን ይችላል። ከዚህ በተጨማሪም ከየት ወደ የት፣ ከምን፣ በምን፣ እስከምን…. ወዘተ” እያልን ነገርን አጥርተን ለነፍሳችንም ለሥጋችንም የሚጠቅመንን መረጃ ልንይዝ ይገባናል።

ከላይ እንደተገለጸው መረጃ ስላገኘን ብቻ የሚያስከትለውን ችግር ሳንረዳ በማኅበራዊ ሚዲያ መልቀቅ በርካታ ችግሮችን በግለሰቦች፣ በቤተሰብ፣ በአካባቢና ብሎም በሀገር ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ጉዳት ከግንዛቤ በማስገባት መዝነን መጠቀም አስፈላጊ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ የምንጠቀምበት ሰዓትም ገደብ ሊኖረው ይገባል። ቀኑን ሙሉ ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ላይ ተጠምዶ መዋልና መከታተል ሱስ እንዳይሆንብንም መጠንቀቅ አለብን።

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።

1 reply

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *