ጽንሰታ ለማርያም

ነሐሴ ፯ ቀን እግዚአብሔር የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤልን ወደ ከበረና ከፍ ከፍ ወዳለ ጻድቅ ኢያቄም ላከው፡፡ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ፅንሰቷንና ልደቷን በእርሱም ለዓለሙ ሁሉ ድኅነትና ተድላ ደስታ እንደሚሆን ነገረው፡፡

ይህ ጻድቅ ሰው ኢያቄምና የከበረች ሚስቱ ሐና ልጅ ሳይወልዱ ሸመገሉ፡፡ የከበረች ሐና መካን ሁናለችና ስለዚህም እጅግ ያዝኑ ነበር፤ የእስራኤል ልጆች ልጅ ያልወለደውን ከእግዚአብሔር በረከትን ያጣ ነው እያሉ ያቀልሉት ነበርና፡፡ እነርሱም ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ዘወትር ፈጽሞ ይለምኑ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ ወንድ ልጅን ወይም ሴት ልጅን ቢወልዱ ለእግዚአብሔር ቤት አገልጋይ ሊያደርጉት ስዕለትን ተሳሉ፡፡ የልቡናቸውን መሻት የሆነውን ልጅ እንዲሰጣቸው እግዚአብሔርን ዘወትር በቤተ መቅደስ ተገኝተው ዕንባቸውን እያፈሰሱ መማጸናቸውን አላቋረጡም፡፡

ከዕለታት በአንድ ቀንም የከበረ ኢያቄምም በተራራ ላይ ሳለ ሲጸልይና ሲማልድ እነሆ እንቅልፍ እንቅልፍ ብሎት ተኛ፡፡ ያን ጊዜ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ተገለጸለት፡፡ እንዲህም አለው፡- “ሚስትህ ሐና ትፀንሳለች ዓለም ሁሉ ደስ የሚሰኝባትን የብዙዎችም ዐይነ ልቡናቸው በእርሷ የሚበራላቸውን በእርሷም ድኅነት የሚሆንባትን ሴት ልጅን ትወልድልሃለች” አለው፡፡

ሐናም በበኩሏ “አቤቱ ጌታዬ የአባቶቼ የእስራኤል አምላክ እኔ ባርያህ እለምንሃለሁ፤ ስማኝ ለዓይኔ ማረፊያ ለልቤ ተስፋ የምትሆነኝ የተባረከች ሴት ልጅ የማኅፀኔን ፍሬ ስጠኝ” ብላ ስትለምን ዋለች፡፡ ርግብ ከልጆቿ ጋር ስትጫወት ዓይታም በተሰበረ ልብ ውስጥ ሆና “አቤቱ ጌታዬ ለዚች ግእዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠህ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሳኸኝ?” ብላ ምርር ብላ አለቀሰች፡፡

ሐና እና ኢያቄም ከካህኑ ዘካርያስ ዘንድ ሄደው “አቤቱ ጌታችን ሆይ ወንድ ልጅ ብንወልድ ተምሮ ቤተ እግዚአብሔርን አገልግሎ እንዲኖር እንሰጣለን፤ ሴት ልጅም ብንወልድ ማይ(ውኃ) ቀድታ፣ መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ፣ ካህናትን አገልግላ እንድትኖር እንሰጣለን” ብለው ስዕለት ገቡ፡፡ ካህኑ ዘካርያስም “እግዚአብሔር ጸሎታችሁን ይስማችሁ፤ ስዕለታችሁን ይቀበልላችሁ፤ የልቡናችሁን መሻት ይፈጽምላችሁ” ብሎ ቡራኬ ሰጥቶ ሸኛቸው።

ሐና እና ኢያቄም ዕለቱን ራእይ ዓይተው አደሩ፡፡ ራእዩም እንዴት ነው ቢሉ፡- ኢያቄም ፯ቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ርግብ ወርዳ በሐና ራስ ላይ ስታርፍ፤ በጆሮዋም ገብታ በማኅፀኗ ስትተኛ አየ፡፡ ሐናም የኢያቄም መቋሚያ ለምልማ አፍርታ ፍጥረት ሁሉ ሲመገባት አየች፡፡ ከዚህም በኋላ ኢያቄም ያየውን ራእይ ለሐና፣ ሐና ያየችውን ራእይ ደግሞ ለኢያቄም በመንገር ራሳቸውን እግዚአብሔር ለገለጸላቸው ነገር ለማዘጋጀት ተስማሙ፡፡

ሁለቱም በአንድ ልብ ሆነው ዕለቱን በሩካቤ ሥጋ አልተገናኙም፤ ፈቃደ እግዚአብሔር ቢሆን ነው ብለው “አዳምንና ሔዋንን ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሉአት ብሎ ያበሰረ አምላክ ለኛስ ይልክልን የለምን?” ብለው ዕለቱን መኝታ ለይተው እስከ ፯ ቀን ድረስ ሰነበቱ፡፡ ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ “ከሰው የበለጠች፤ ከመላእክት የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላችሁ” ብሎ ለሐና ነገራት፡፡

በፈቃደ እግዚአብሔር፣ በብሥራተ መልአክ እመቤታችን እግዝእትነ ማርያም ነሐሴ ፯ ቀን ተፀነሰች፡:

ቅዱስ ያሬድ “ማርያምሰ ተኀቱ እምትካት ውስተ ከርሱ ለአዳም ከመ ባሕርይ ጸዓዳ፤ ማርያምስ ከጥንት ጀምሮ በአዳም ባሕርይ ውስጥ እንደ ነጭ ዕንቁ ታበራለች” በማለት እንደተናገረው እግዚአብሔር ቅድስት ድንግል ማርያምን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ድኅነት መሠረት እንዳደረጋት፣ ሊመረመር በማይችል ጥበቡም እንዳዘጋጃት ተናግሯል፡፡ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ “ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤   በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ” ብሎ አመስግኗታል፡፡

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን መሠረት አድርጋ ዕለቱን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምልጃዋ በረከቷ በሁላችን ላይ ይደር፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስንክሳር ነሐሴ ቀን

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *